ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን (ለህጻናት)

በአዜብ ገብሩ

 

በአንድ ወቅት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤተ መቅደስ ሄደ፡፡ በቤተ መቅደስ ውስጥም በሬዎችና በጎችን፣ ርግቦችንም ሲሸጡ አገኘ፡፡ በዚህን ጊዜ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጣም አዘነ፡፡ የገመድ ጅራፍም አበጀ፡፡ በጎችንና በሬዎችን፣ ሁሉንም ከቤተ መቅደስ አስወጣ፡፡ “ቤቴ የጸሎት ቤት እንጂ የንግድ ቤት አይደለችም” አላቸው፡፡

ልጆች ጌታ እነዚህ ሰዎች በቤተ መቅደስ የማይሠራ ሥራ ስለሠሩ እንዴት እንዳዘነ አያችሁ? ቤተ ክርስቲያንን ስናከብር ጌታችን በእኛ ደስ ይለዋል፤ የምንፈልገውንም ነገር ይሰጠናል፡፡ ስለዚህ ልጆች እኛም ወደ ቤተ ክርስቲያን ስንሄድ እግዚአብሔርን እንዳናሳዝነው ሥርዓትን መጠበቅ አለብን፡፡

1.ወደ ቤተ ክርስቲያን ስንገባ ተሳልመን መግባት፣
2.የተቀደሰ ቦታ ስለሆነ ጫማችንን ማውለቅ፣
3.በጸጥታ ሆነን ሥርዓቱን መከታተል
4.መጸለይና እግዚብሔርን ማመስገን አለብን፡፡

 

ልጆች በቤተ ክርስቲያን ስትሆኑ ይህን ማክበር አለባችሁ ማለት ነው፡፡ ሌሎች ልጆችም ሲያጠፉ ስታዩ ምከሯቸው፡፡ ለምሳሌ፡- ድምጻቸውን ከፍ አድርገው ሲያወሩ፣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሲመገቡ ብታዩ፣ በቅደሴ ጊዜ ያለ አግባብ ከቦታ ቦታ ሲዘዋወሩ ተው ልትሏቸው ይገባል፡፡
እንግዲህ ልጆች የአግዚአብሔር ቤት ስለሆነች ቤተ ክርስቲያንን ልትወዷት ይገባል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያለውንም ሥርዓት ሁሉ ልትፈጽሙ ይገባል፡፡ ይህን ካደረጋችሁ አግዚአብሔር ደስ ይለዋል፤ እናንተንም ይወዳችኋል፡፡

 

ደህና ሰንብቱ እሺ ልጆች!