ልጆች በቤተክርስቲያን

       በአዜብ ገብሩ

“ልጆቼ ኑ ስሙኝ እግዚአብሔርን መፍራት አስትምራችኋለሁ፡፡” መዝ 34÷11

ልጆች እንደምን ሰነበታችሁ? ዛሬ ቤተክርስቲያን ውስጥ ስንሆን ምን ማድረግ ምን ደግሞ አለማድረግ እንደሚገባን የሚያሳየን ታሪክ ይዘን ቀርበናል፡፡ በደንብ ተከታተሉን፡፡

በድሮ ዘመን ደብረ ቀልሞን በምትባል አካባቢ የሚገኙ ሕፃናት ቅዳሴ ሊያስቀድሱ ወደ ቤተክርስቲያን ሄዱ፡፡ በቅደሴ ጊዜም ወዲያና ወዲህ እያሉ ቅደሴ ሲረብሹ እግዚአብሔር በጣም አዘነባቸው፡፡ ከዚያም እነዚህ ያጠፋት ልጆችን እንዲቀጡ መላእክትን ከሰማይ ላከ፡፡ የተላኩትም መላእክት በታዘዙት መሠረት ያጠፉትን ልጆች እንዲቀጡ መላእክትን ከሰማይ ላከ፡፡ የተላኩትም መላእክት በታዘዙት መሠረት ያጠፉትን ልጆች ቀጥተው ሲመለሱ ከተላኩት መላእክት አንዱ ግን ልጆቹን በሚቀጣበት ሰዓት አንድ የሚያምር ልጅ አጋጠመውና አዘነለት፡፡ “ይህንንስ የፈጠረው ይቅጣው” ብሎ ተወው፡፡ ይህን በማድረጉና የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ በመተላላፉ መልአኩ እንደሌሎች መላእክት ወደ ሰማይ ለማረግ አልቻለም፡፡ በዚያ ወድቆ ሳለ አንድ ዲያቆን ለአገልግሎት ወደ ቤተክርስቲያን ሲገባ አገኘው፡፡ ተጠግቶም “አንተ ምድራዊ ነህ ወይስ ሰማያዊ” ብሎ ጠየቀው፡፡ መልአኩም “ሥራዬ ምድራዊ አደረገኝ እንጂ ተፈጥሮዬስ ሰማያዊ ነው፡፡ ሄደህ ለካህኑ ንገርልኝና ይደልይልኝ፡፡” አለው፡፡ ዲያቆኑም ሄዶ ለካህኑ ነገረው፡፡ ካህኑም ከሥዕለ ማርያም ሥር ተደፈቶ እመቤታችንን እየተማፀነ ጸለየለት እመቤታችንም ከሥዕሏ ላይ ተገልጻ “በቀኝ እጅህ ቀኝ ክንፉን በግራ እጅህ ግራ ክንፉን ይዘህ በፈጣሪ በእግዚአብሔር ስም ተነሥ በለው” አለችው፡፡ ካህኑም እንደታዘዘው አደረገ፡፡ መልአኩም ኃይሉ ተመለሰለትና ወደ ሰማይ ዓረገ፡፡

አያችሁ ልጆች በቤተክርስቲያን ውስጥ ወዲህ ወዲያ ማለት፣ መረበሽ ማውራት ቅጣት ያስከትላል፡፡ እንደውም ልጆቹ ባጠፉት ጥፋት ቅጣቱ ለመልአኩም ተርፎት ነበር፡፡ እመቤታችን ከፈጣሪ አማልዳ መልአካዊ ኃይሉን ባታስመልስለት ኑሮ በጣም አሳዛኝ ሁኔታ ላይ ወድቆ ነበር፡፡ ስለዚህ ልጆች ወደ ቤተክርስቲያን ስትሄዱ ጥንቃቄ አይለያችሁ እሺ ገላችሁን ታጥጣችሁ፣ የታጠበ ንጹሕ ልብስ ለብሳችሁ፣ ነጠላችሁን መስቀለኛ ለብሳችሁ፣ ቅዳሴ ከመጀመሩ በፊት በቤተክርስቲያን ተገኝታችሁ፣ ወደቁርባን ስትቀርቡ በሥርዓቱ ሳትጋፉ ተራ ጠብቃችሁ መቁረብ ይገባል፡፡ አንግዲህ ልጆች ከዚህ ታሪክ ትምህርት በማግኘት እናንተ ሥርዓት አክባሪና ጨዋ ልጆች ሆናችሁ ለሌሎች ልጆች እንደምትመክሩና እንደምታስተምሩ ተስፋ እናደርጋለን፡፡ በሉ ደህና ሁኑ ልጆች፡፡