“ሕፃናት ወደኔ ይመጡ ዘንድ አትከልክሏቸው” ሉቃ.18÷16 (ለሕጻናት)

በአዜብ ገብሩ

ግንቦት 20፣ 2003ዓ.ም

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ደህና ናችሁ? በዛሬው ጽሑፋችን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሕፃናትን ምን ያህል እንደሚወድ የሚያስረዳ ጽሑፍ ይዘን ቀርበናል÷ በደንብ አንብቡት እሺ፡፡

በአንድ ወቅት ጌታችን ለምለም የሆነ ሣር ባለበት ቦታ ላይ ብዙ ሰዎች በዙሪያው ከበውት ቆመው ያስተምራቸው ነበር፡፡ ሰዎቹም የእርሱን ጣፋጭ የሆኑ ቃላት ለማዳመጥ ከተለያየ ቦታ የተሰበሰቡ ነበሩ፡፡ ሁልጊዜ ከጌታ የማይለዩት ዐስራ ሁለቱ ሐዋርያትም በዚያ ነበሩ፡፡ እነዚህ ዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ጌታ በሄደበት ቦታ ሁሉ ይሄዳሉ፤ ከእርሱ ጋር ይጸልያሉ፤ እርሱንም ያገለግሉታል /ይታዘዙለታል/፡፡ ታዲያ ልጆች ጌታችን ቁጭ ብሎ የተሰበሰቡትን ሕዝብ እያስተማረ ሳለ ልክ እንደ እናንተ ሕፃን የሆነ ልጅ ወደ ጌታችን እየሮጠ መጣ፡፡ እንዲህም አለው “ኢየሱስ ክርስቶስን ማየት እፈልጋለሁ አለ፡፡” ከዚያም ዘወር ሲል እንደ ፀሐይ የሚያበራውን የጌታችንን ፊት አየ፤ ጣፋጭ የሆነውንም የጌታችንን ድምጽ ሰማ፡፡ ጌታችንም የሕፃኑን እጅ ይዞ “ከእኔ ጋራ ና” አለው፡፡ ወደ ሐዋርያትም ዘወር ብሎ እንዲህ አላቸው፡፡ “በመንገድ ሳለን ስለምን ትከራከሩ ነበር?” እነርሱም ዝም አሉ፡፡ ምክንያቱም በመንገድ ሳሉ ከእኛ መካከል ከሁላችን የሚበልጥ ትልቅ ማነው? እያሉ ይከራከሩ ስለነበር ነው፡፡ ጌታችን ለጥቂት ጊዜ ዝም ብሎ ከቆየ በኋላ ሕፃኑን “ወደ እኔ ና” አለው ሕፃኑም ወደ ጌታችን ተጠጋ፡፡ ጌታችንም ሕፃኑን አንስቶ አቀፈው፡፡ ለሐዋርያቱም እንዲህ አላቸው “ከእናንተ መካከል ከሁላችሁ የሚያንስ እርሱ ከሁላችሁ ይበልጣል፡፡” ሐዋርያትም ጌታችንን በትኩረት ይሰሙት ነበር፡፡ የሚናገረውንም ቃል ለመረዳት ይሞክሩ ነበር፡፡ ሕፃኑ ልጅ ግን ጌታችንን የተናገረውን እንዲያስረዳው ጠየቀው ጌታችንም “ሕፃናትን ወደ እኔ ይመጡ ዘንድ ተዉአቸው÷ አትከልክሏቸውም፤ የእግዚአብሔር መንግሥት እንደ እነርሱ ላሉት ናትና አለ፡፡”

ልጆች ጌታችን እንዴት እንደሚወዳችሁ አያችሁ? እናንተም ትወዱታላችሁ አይደል አዎ በጸሎታችሁ ወቅት ጌታን እንደምትወዱት ልትነግሩት ይገባል፡፡ እርሱ የሚወደውንም መልካም ሥራ ልትሠሩ ይገባል፡፡ ልትነግሩት ይገባል፡፡ ከጓደኞቻችሁ ጋር ሳትጣሉ በፍቅር ልትኖሩም ይገባል፡፡ ይህን ካደረጋችሁ ጌታችን እጅግ በጣም ይወዳችኋል፡፡ ሁሌም ከእናንተም ጋር ይሆናል ማለት ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር