ዓሣ

ወርቅ ሠሪው ጴጥሮስ(ለሕፃናት)

በእመቤት ፈለገ

ልጆች እንደምን ሰነበታችሁ? ዛሬ ይዘንላችሁ የቀረብነው የአንድ ጌጣጌጥ የሚሠራ ሰው ታሪክ ነው ተከታተሉ፡፡

ከብዙ ዓመታት በፊት ስሙ ጴጥሮስ የተባለ በጣም ጥሩ ክርስቲያን ነበር፡፡ የተለያዩ ጌጣጌጦች ማለትም ቀለበት፣ የአንገት ሃብል ይሠራ ነበር፡፡

ብዙ ጊዜም ቤተ ክርስቲያን መሄድ ያስደስተው ነበር፡፡ እርሱ በሚኖርበትም አካባቢ የሚገኝ በእግዚአብሔር የማያምን አንድ መጥፎ ሰው ነበር፡፡ ጴጥሮስንም እጅግ በጣም ይጠላው ነበር፡፡ ባገኘው አጋጣሚ ሁሉ ሊጎዳው ይፈልግ ነበር፡፡ ምክንያቱም ጴጥሮስ እግዚአብሔርን ስለሚወደው ነበር፡፡ ይህ ክፉ ሰው የአንድ የመንግሥት ባለሥልጣን ጸሐፊ ነበር፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን የመንግሥት ባለሥልጣን የነበረው ሰው ቀለበት ማሠራት ፈለገ እንዲያሠራለትም ለዚያ ክፉ ሰው ሰጠው፡፡ ያ መጥፎ ሰውም ጴጥሮስን ለመጉዳት ጥሩ አጋጣሚ እንዳገኘ አሰበና ደስ አለው፡፡ ወደ ጴጥሮስም ሄደና ቀለበቱን ሰጠው፡፡ የመንግሥት ባለሥልጣኑ ቀለበት እንደሆነ ቆንጆ አርጎ በፍጥነት እንዲሠራ ነገረው፡፡ ጴጥሮስም ቀለበቱን ተቀብሎ ጠረጴዛ ላይ አስቀመጠውና ሌላ እንግዳ ማስተናገድ ጀመረ፡፡ ክፉውም ሰው ቀለበቱን ሰርቆ ሄደ ወንዝ ውስጥ ጣለው፡፡ ጴጥሮስ ቀለበቱን ሲፈልግ አጣው በጣም አዘነ የመንግሥት ባለሥልጣኑም ይህን ሲሰማ ምን ሊያደርገው እንደሚችል አሰበ እጅግ ጨነቀው ሱቁንም ዘግቶ ወደ ቤቱ ሄደ፡፡

ቤቱ እንደገባም የሆነውን ሁሉ ለባለቤቱ ነገራት እርሷም እግዚአብሔር ከነርሱ ጋር እንደ ሆነ ምንም መፍራት እንደሌለበት ነገረችው፡፡ በሚቀጥለውም ቀን ወደ ሥራ ሄደ ነገር ግን በጣም ስለተጨነቀ ምንም ሥራ መሥራት አልቻለም፡፡ ዓሣ የሚሸጥ ሰው በየቀኑ ለጴጥሮስ ዓሣ ይዞለት እየመጣ ይሸጥለት ነበር፡፡ ያን ቀን ግን ጴጥሮስ ዓሣ ሻጩን ሲያየው “ዛሬ ምንም አልፈልግም አለው፡፡ ዓሣ ሻጩም ጥሩ ዓሣ እንደያዘ ነገረው ጴጥሮስ ግን “በፍጹም አልገዛም” አለው፡፡ ዓሣ ሻጩም ወደ ጴጥሮስ ቤት ሄደ ዓሣውን ለሚስቱ ሸጠላት፡፡

ዓሣየጴጥሮስ ሚስትም ዓሣውን ገዝታ መሥራት ስትጀምር በጣም የሚያብረቀርቅ ነገር አየች ቀለበት ነበር! ልክ ባለቤቷ ወደ ቤት ሲመጣ የተፈጠረውን ነገር ማመን አቃተው፡፡ እግዚአብሔር ሕይወቱን ጠበቀለት፡፡

ጴጥሮስን ከክፉ ነገር ሁሉ የጠበቀው አምላክ እኛንም ከክፉ ነገር ይጠብቀናል፡፡ ስለዚህ ልጆች ሁል ጊዜም ስለሚደረግልን ነገር ሁሉ እግዚአበሔርን ማመስገን አለብን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔ

በደህና ሰንብቱ ልጆች!