ወጣትነትና ፈተናዎቹ

የወጣትነትን የዕድሜ ክልል በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አስተምሮ መሠረት ከሃያ እስከ ዓርባ ዓመት ያለው ዕድሜ ነው፡፡

እንደሚታወቀው የሰው ልጅ ተፈጥሮ ከአራቱ ባሕርያተ ሥጋ ማለትም ከነፋስ፤ ከእሳት፤ ከውሃና፤ ከመሬት ሲሆን አምስተኛ ነፍስን ጨመሮ እነዚህ በአንድ ሰው የሕይወት ዘመን ላይ ሲንጸባረቁ ይኖራሉ፡፡ የሰው ልጅ በሚሞትበት ጊዜ አራቱ ባሕርያት ወደነበሩበት ጥንተ ህላዌ ይመለሳሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ሥጋ ይበሰብሳል ይፈርሳል፡፡ በትንሣኤ ዘጉባኤ ደግሞ አራቱም ባሕርያት ከነፍስ ጋር እንደገና  ተዋሕደው ይነሣሉ፡፡ አራቱን ባሕርያተ ሥጋ ረቂቃን ግዙፋን (ክቡዳን ቀሊላን) ብለን እንጠራቸዋለን፡፡ የሚገርመው ክቡዳኑን ከላይ ቀሊላኑን ከታች አድርጎ ነው ያስቀመጣቸው፡፡ እርስ በእርሳቸው ተጠባብቀው እንዲኖሩ አደረጋቸው ምክንያቱም ክቡዳኑ ከላይ ሆነው እንዲጠብቋቸው ነው ቀሊላኑ ግን ከላይ ቢሆኑ ኖሮ ሽቅብ ይሄዱ ነበር ክቡዳኑም ከታች ቢሆኑ ኖሮ ቁልቁል ሲሔዱ በኖሩ ነበር፡፡ ተሸካክመው የሚኖሩት ምሳሌነቱም አራቱ ባሕርያተ ሥጋ ተቻችለው እንደሚኖሩ እኛም ከኛ በላይ ያሉ እንዳሉ በማወቅ ተቻችለን እንድንኖር ነው፡፡ የመሬት መሠረቷ ጽናቷ ነፋስ ነው፡፡ የእኛም ከላይ ሥጋችን መሬት ነው፡፡ መሬትም በውኃ ላይ ናት ይህም ውሃው ደማችን ነው፡፡ የእኛም ሥጋችን በደማችን ነውና የሚጸናው የውሃዎች ሕይወት ነፋስ ነው ውሃው ንጹሕ አየር ከሌለው ይበከላል፡፡ አበው ከአፋፍ ላይ ነፋስ ከአፍ ላይ እስትንፋስ እንዲሉ የሰው ልጅም ሁሉ በዘመኑ ሲተነፍስ ይኖራልና፡፡ የሰው ልጅ የሰውነት ሙቀት ባሕርየ እሳት ለመኖሩም በቂ ማስረጃ ነው፡፡

ከሃያ እስከ አርባ ያለው የዕድሜ ክልል የእሳት ባሕርይ ጎልቶ የሚታይበት ነው፡፡ ይህም ዘመነ እሳት ወይም ምግበ እሳት ይባላል፡፡ ይህም ሰውን ወጣት የሚያሰኘው ዘመን ነው፡፡

በዚህ የወጣትነት ዘመናችን ጥሩና ታላቅ መሆን ካልቻልን የምናጣው ክብርን ብቻ ሳይሆን ማንኛውንም ኃላፊነት ጭምር እናጣለን፡፡ እንደ ኤሳው ስንሆን እንደ ያዕቆብ ያለ ታናሽ ወንድምህ ብኵርናህን ይወስድና አንተ የእሱን እጅ ስታይ ትኖራለህ፡፡ እንዲሁም ታናናሾችህን የመቅጣትና የመገሠጽ መብት አይኖርህም፡፡ አላዋቂ ጎልማሳ ወጣቶችን መገሠጽ እንደማያምርበት ሁሉ አንተ ሕገ ወጥ ወጣት ሆነህ ታናናሾቼን ልቅጣ ልምከር ብትል ማንም አይሰማህም፡፡ ምክንያቱም (ማቴ. ፯፥፭) ላይ አንተ ግብዝ አስቀድመህ ከዓይንህ ምሰሶውን አውጣ፡፡ ከዚያ በኋላ ከወንድምህ ዓይን ጉድፉን ታወጣ ዘንድ አጥርተህ ታያለህ ስለተባልን ይህ በእንዲህ እንዳለ የሰው ልጅ ከልጅነት ወደ ወጣትነት በሚሸጋገርባቸው ወራትና ዓመታት አካላችን እንደሚደራጅና አእምሮአችን እንደሚዳብር ሁሉ ምኞታችንም በዓይነትና በመጠን እየሰፋና እየጨመረ ይሄዳል፡፡ ይህ የወጣቶች ምኞት በአመዛኙ ከመንፈሳዊነት ጋር የሚቃረን ይሆናል፡፡ እንዲሁም በጎልማሶች ላይ የሚከሰተውን ምኞት አስመልክቶ ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ (በ፪ኛ ጢሞ. ፪፥፳፪) ላይ ከክፉ የጎልማሳነት ምኞት ግን ሽሽ ብሎናል፡፡ በእርግጥም በወጣትነት ዘመን የሚገኝ ምኞት እጅግ ክፉ ነው ወጣትነት የሚሠራበት ዘመን እንጂ ክፉ ምኞት የሚመኙበት ዘመን አይደለም፡፡

ወጣቶችና ጾሮቻቸው (ፈተናዎቻቸው)

ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ በመልእክቱ ፩፥፲፬ ላይ «ሰው ራሱ በገዛ ምኞቱ ሲሳብና ሲታለል ይፈተናል» በማለት እዳስተማረን፤ በወጣትነት ዘመን የሚገኝ ምኞት ከመጠን በላይ ወደ ጥፋት የሚስብ የሚጎትትና የሚያታልል ነው፡፡ በተለይ ሰው በገዛ ምኞቱ ሲሳብ በወጣትነት ዘመን ምንም አእምሮው የበሰለ ቢሆንም እንኳ ራሱን መግዛት ካልቻለ በብዙ ነገር ይፈተናል በዚህም ወጣቶች ከሚፈተኑባቸው መንገዶች መካከል ዝሙትና ትውዝፍት (የምዝር ጌጥ) መውደድ ነው፡፡ እንዲሁም የወጣቶች ልዩ ልዩ ጾር (ፈተና) ቢኖሩም እነዚህ ዐበይት ጾሮች የኃጢአት መንገድ ጠራጊ ይሆናሉ፡፡

መፍትሔዎች

  • ራስን መግዛት

ይህ ማለት ፍቃደ ሥጋን ለፍቃደ ነፍስ ስናስገዛ፤ በዚህም ሕገ እግዚአብሔርን ስንጠብቅ፤ ራሳችንን ሆነን በተማርነው መኖር ስንጀምር፤ ልማድ የሆነብንን ድርጊት አስወግደን በተቀመጠልን ትእዛዝ ስንኖር እና ሁለንተናችንን ለእግዚአብሔር ስናስገዛ ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት (በመዝ. ፪፥፩) ላይ በፍርሀት በመንቀጥቀጥ ተገዙ ስላለን በመገዛት ውስጥም የማያቋርጥ ዘለዓለማዊ ደስታ እንዳለ አውቀን ራሳችንን መስለን መኖር እንችላለን፡፡ ስለዚህ ነው ቅዱስ ጳውሎስ ለመንፈስ ልጁ ለጢሞቴዎስ (፩ኛ ጢ. ፫፥፭) ላይ ቤቱን ማስተዳደር የማይችል የእግዚአብሔርን ቤት ሊመራ እንደማይችል ሁሉ ሌሎችን ማስተዳደር የምንችለው ራሳችንን ስንገዛ፤ ስንገራና ስንቆጣጠር እንደሆነ ነግሮናል፡፡ እንዲሁም ኖኅን ስንመለከት (ዘፍ. ፮፥፩) ላይ ከነቤተሰቡ ራሱን ገዝቷል፡፡ ሌሎችን ለመናገርና ለመውቀስ መርከቧን በመሥራት፤ አራዊትን፤ እንስሳትንና አዕዋፍን ሁሉ መግዛት ችሏል፡፡ ራስን መግዛት ማለት ቤተ ክርስቲያን ገብተን እስክንወጣ፤ ትዳር እስክናገኝ፤ ሥራ እስክንይዝና እና የፈለግነው ነገር ሁሉ እስኪሳካልን ድረስ አይደለም፡፡ ነገር ግን ራስን መግዛት ማለት መፍረድ ሲቻል አለመፍረድ፤ ማድረግ ሲቻል አለማድረግ ልክ እንደ ዮሴፍ (ዘፍ. ፴፱፥፩) ጀምሮ ሁሉ ሲቻል መተው እንዲሁም ልክ ይሁን አይሁን በነገሮቻችን ሁሉ ራሳችንን ስንገዛ በአጠቃላይ ከአላስፈላጊ የሥጋ ጠባይዓት ሁሉ መራቅ ስንችል ራሳችንን ገዝተናል ማለት እንችላለን፡፡

  • ራስን ማወቅ

ለራሳችን ያለንን አመለካከትና ጠባይ በአጠቃላይ ከሌሎች ሰዎች የሚለየንንና የሚያመሳስለንን ማንነት በመረዳት በዓላማ መኖር ስንችል ራሳችን ማወቅ ቻልን ማለት ነው፡፡ ይህም ሰው ጠንካራና ደካማ ጎኑን ማወቅ ከቻለ በሥጋዊና በመንፈሳዊ ሕይወት አዎንታዊ አስተዋጽዖ ለማበርከትና ዓላማውን ከግቡ ለማድረስ የሚያስችለውን እውቀት ያገኛል፡፡ ሙሴ (በዘፀ. ፬፥፲) ላይ ጌታ ሆይ እኔ አፌ ኮልታፋ ምላሴም ጸያፍ የኮነ ሰው ነኝ ብሎ ነው የተናገረው፡፡ ሆኖም ሙሴ በውስጡ ያለውን ጠንካራ ጎን አልተመለከተም፡፡ ራሱን የሚያውቅ ሰው ለራሱ ሕይወት ኃፊነት ይወስዳል ሌላ ሰው እንዲንከባከበው አይጠይቅም፡፡ በጉብዝናው ወራት ገደል አለ ከተባለ ይሰማል፤ ገደሉ እንደሚጎዳው ስለሚያውቅ፤ ሕይወቱን ለአደጋ አያጋልጥም፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ በመልዕክቱ (፪ኛ ጴጥ. ፩፥፭-፮) ላይ በእምነታችሁ በጎነትን ጨምሩ፤ በበጎነትም እውቀትን፤በእውቀትም ራስን መግዛት፤ ራስን በመግዛትም መጽናትን በመጽናትም እግዚአብሔርን መምሰልን ነግሮናልና፡፡ ስለዚህ ይህን በማድረግ ለሕይወታችን ኃላፊነትን እንወስዳለን፡፡

ራሱን የሚያውቅ ሰው ሰብእናውን ያከብራል፤ ለምን ዓላማ እንደተፈጠረ በመረዳት ሰብእናውን ጠብቆ በደስታ ይኖራል፤ በራሱም ይተማመናል፡፡ የሚያውቀውን በአግባቡ ይናገራል፤የማያውቀውን ይጠይቃል፤ ድክመቱን ሲነግሩት በአዎንታዊ መንገድ ይቀበላል፤ ማንነቱን በቦታና በጊዜ ራሱን አይለዋውጥም የጸና ግንብ ነው፤ በዐለት ላይ ተመሥርቷልና፡፡ ከሐሜት ይርቃል፤ በግልጽ መወያትን ያዘወትራል፤ ለውድቀቱም ራሱን ተጠያቂ ያደርጋል፤ ሌሎቹን ተጠያቂ አያደርግም፤ ለውድቀት በቀላሉ እጁን አይሰጥም የሚጓዝበትን ያውቃልና፡፡ ካለፈው የወጣትነት ሕይወቱ ልምድ በመውሰድ አሁን ያለበትን ሁኔታ በመረዳት ሥጋዊና መንፈሳዊ ሕይወቱ ወዴት ሊያመራ እንደሚችል አስቀድሞ ይዘጋጃል፡፡ ይህም የዛሬ ማንነቱ ለነገ ዘለዓለማዊ ሕይወቱ መሠረት መሆኑን በመረዳት ጠንክሮ በመንፈሳዊ ሕይወቱ ይተጋል፡፡ በመጨረሻም ራሱን የሚያውቅ ወጣት ለመንፈሳዊ ሕይወቱ መሳካት አስፈላጊውን መሥዋዕትነት ይከፍላል፡፡ ራሱን ያላወቀና ያልገዛ ወጣት ዓላማውን ይስታል፤ ለራሱም ለሌሎችም መሆን አይችልም፡፡

ስለዚህ በወጣትነት ዘመናችን ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚያቀርበንን እንጂ የሚያርቀንን ነገር እንድንሠራ አይጠበቅብንም፡፡ እኛ ራሳችንን አድነን ሌሎችን በማዳን ክርስቲያናዊ ግዴታችንን መወጣት ይጠበቅብናል፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ከሰኔ ፩-፲፭ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም

ክርስቲያናዊ ሕይወት

ዲያቆን ዮሴፍ በቀለ

በክርስቲያናዊ ሕይወት ውስጥ መልካም ሥራ ሁልጊዜ ይኖራል፤መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ   በትምህርተ ወንጌል እንዳስተማረን  ድኅነትን የምናገኝው በሕገ እግዚአብሔር ጸንተን ስንኖር እንደሆነ ነግሮናል። የሰው ሕይወቱ የጸጋ ነው፤ በፈቃዱ በሁለት ሞት ነፍሱን/ሕይወቱን/ ይነጠቃል፡፡ የመጀመሪያው ሞት የማይቀር ሲሆን የሁለተኛው ሞት ግን በሕገ እግዚአብሔር ለልደተ ነፍሳት የተሰጠ ነው፤ ራዕ. (፪፥፲፩)፤ ሕያው የሆነ ሰው እንጂ ሕይወት የሆነ ሰው የለምና፡፡

ስለሆነም ለዘለዓለም በሕይወት ለመኖር ይቻለን ዘንድ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምድር ላይ በቆየበት ጊዜ ያደረገውን ተአምር፤ ያስተማረውን ወንጌልና  ለእኛ የገለጸልንን ፍቅር መሠረት አድርገን መመራት ይጠበቅብናል። ይህንንም በተግባር ለመፈጸም የሚከተሉትን ምግባሮች ማከናወን አለብን፡፡

፩.አገልግሎት

ከሁሉም አስቀድሞ የሰው ልጅ ዕለት ዕለት ፈጣሪውን ሊያመሰግን ይገባል፤ ይህም መጸለይ፤መጾም፤ማስቀደስና መዘመር ይገባዋል፡፡ ከዚህም ባሻገር ነዳያንን ማብላትና ማጠጣት በጉልበትና በሙያ አድባራትን ማሰራት ከአንድ ክርስቲያን የሚጠበቅ ሲሆን አሁን አሁን ግን የምንመለከተው እንደዚህ አይደለም፡፡ የዛሬ ፲ ዓመት ሰንበት ተማሪ የነበረው ልጅ ከዓመት በኋላ የመድረክ ዘፋኝ ይሆናል፤ የዛሬ ፭ ዓመት ሰንበት ትምህርት ቤት ድራማ ይሰራ የነበረው ሰው በኋላ ተለውጦ ሌላ ታሪክ ውስጥ ይገባል፡፡ የሰንበት ትምህርት ቤት ሰብሳቢ፤ ጸሓፊና አባል የነበረው፤ ሚስት ሲያገባ ያንን ሁሉ እርግፍ አድርጎ ይተወዋል፤ ትዳር እኮ የአገልግሎት ጡረታ አይደለም፤ አንዴ ካገቡ አይመለሱም፡፡

ሰንበት ተማሪ ሆኖ ቤተክርስቲያንን እያገለገለ እስከ ሕይወቱ መጨረሻ ዘማሪ፤ ካህን፤ ዲያቆን ወይም ሰባኪ ሆኖ ገዳማትን እያሰራ፤ ነዳያንን እያበላ፤ ጉባኤ እያዘጋጀ፤ ጽዋ ማኅበራትን እየመራና ወዲህ ወዲያ ሳይል፤ ታመምኩ፤ ተቸገርኩ፤ ምስጋና ቢስ ነኝ፤ እጄን በቆረጠው ሳይል የሚኖር ማን ነው? አንዳንዶች ደከምን ብለው አገልግሎትን  የሚተው አሉ፡፡ ታማን ብለን የምንተውም አለን፤ ይህቺን ካልታገስን ታዲያ ስለ ዲዮቅልጥያኖስ ዘመን ለምን እናወራለን? እስከ መጨረሻው የትኛው ሰው ነው የሚጸናው? በክርስቲያናዊ ሕይወት እስከ መጨረሻዋ ዕለት መጽናት ያስፍልጋል፡፡

.ጊዜን ማክበር

ጊዜ ከእግዚአብሔር የተሰጠን ስጦታ ነው፤ እናም በአግባቡ ልንጠቀምበት ያስፈልጋል፡፡ ጉባኤ ላይ በመገኘት፤ ሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ በማገልገል፤ ድሆችን በመጎብኘት፤ ሕመምተኞችን በመጠየቅ፤ ገዳማትንና አድባራትን ለማሰራት በመድከም፤ መምህራኑ ሲያስተምሩና መዘምራኑ ሲዘምሩ በማገልገል ጊዜን ማክበር ያስፈልጋል፡፡ በማቴዎስ ወንጌል  (፳፭፥፴፬-፴፮) ላይ እንደተገለጸው «እናንተ የአባቴ ቡሩካን፤ ዓለም ሳይፈጠር የተዘጋጀላችሁን መንግሥት ትወርሱ ዘንድ ኑ። ተርቤ አብልታችሁኛልና፤ተጠምቼም አጠጥታችሁኛልና፤ እንግዳም ሆኜ ተቀብላችሁኛልና፡፡ ታርዤ አልብሳችሁኛልና፤ ታምሜም ጎብኝታችሁኛልና፤ ታስሬም ወደ እኔ መጥታችሁ  ጠይቃችሁኛልና» ይለናል።

መጠቀም ያለብን ትርፍ ጊዜያችንን አይደለም፤ ያለንን ጊዜ መስጠትና ሙሉ ጊዜን መስጠት ይለያያሉ፤ በወንጌል እንደተጠቀሰው አንድ ሰው ከሞላው ከኪሱ አፈሰና ሰጠ፤ አንዲት  ምስኪን መበለት ደግሞ ሁለት ሳንቲም ነበራትና እሱን ሰጠች፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእነዚህ ሰዎች ሁሉ ይህቺ ጸደቀች አለ፡፡ በሉቃስ ወንጌል (፳፩፥፫-፬) ላይ እንደተናገረው «እውነት እላችኋለሁ፥ይህቺ ደሃ መበለት ከሁሉ ይልቅ አብዝታ ለእግዚአብሔር መባ አገባች፡፡ እነዚህ ሁሉ ከተረፋቸው ለእግዚአብሔር መባ አግብተዋና፤ ይህች ግን ከድህነቷ ያላትን ጥሪቷን ሁሉ አገባች»፡፡ካለን እንድንሰጥ ነው እንጂ ሲተርፈን፤ ሥራ ሠርተን፤ በልተን፤ ጠጥተን፤ተዝናንተን ስንጨርስ መጨረሻ ላይ የት ልሂድ ብለን ቤተክርስቲያን የምንሄድ ከሆነ ይህ ለጊዜ ዋጋ መስጠት አይደለም፡፡ በጊዜያችን ተጨማሪ ልንሰራበት የምንችለውንና ገንዘብ የምናገኝበትን፤ ሰው ቤት ሄደን ጥዑም ምግብ ተመግበን የምንጠጣበትን ጊዜ ሰውተን፤ እንደ አስፈላጊነቱ ስንሰጥ ለጊዜ መሥዋዕት አደረግን ይባላል፤ሲተርፍ መስጠት ዋጋው ትንሽ መሆኑን ወንጌልም ነግሮናልና፡፡

፫. በሃይማኖት መጽናት

በዮሐንስ ራእይ ፲፪፥፲፮-፷ እንደተጠቀሰው ዘንዶው በሴቲቱ ላይ ተቆጥቶ የእግዚአብሔርን ትእዛዛት የሚጠብቁትን የኢየሱስ ምስክር ያላቸውን ከዘሯ የቀሩትን ሊወጋ ሄደ ይላል፡፡ ከዘሯ የቀረነውን የኢየሱስ ክርስቶስ ምስክርነት ያለንን ሊዋጋ ከተነሣው ዘንዶ ጋር ታግሎ ሃይማኖትን መጠበቅ ተገቢ ነው፤ በዚህ ዘመን ሃይማኖት ጸንቶ ሃይማኖትን መጠበቅና ከመናፍቃን ጋር መዋጋት የክርስቲያን ኃላፊነት ነው፤ ይሁዳ (፩፥፫) «ለቅዱሳን የተሰጠችውንም ሃይማኖት ትጋደሉላት ዘንድ አማልዳችኋለሁ» ይላል።

ስለ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መጋደል ክርስቲያናዊ ምግባር ነው፤ ብዙዎቹ ዛሬ በገንዘብና ከንቱ በሆነ ነገር ይታለላሉ፤ ቅዱስ ጳውሎስ እንደተናገረው «ለዚህ ዓለም ስሕተት፥ በክርስቶስ ሕግ ያይደለ፥ በሰው ሠራሽ ሥራዐት ለከንቱ የሚያታልሉ ሰዎች በነገር ማራቀቅ እንዳያታልሉአችሁ፥ተጠንቀቁ» (ቈላ. ፪፥፰)፡፡ በሰይጣን በመታለል ሃይማኖታቸውን የሚለውጡ አሉ፤ ጌታችን በማቴ. (፳፬፥፲፫) ላይ «እስከ መጨረሻው የሚታገሥ ግን እርሱ ይድናል» ብሏል፡፡

፬.እራሳችንን ከፍትወት መጠበቅ

 ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ በዚህ ዘመን ራሳችን ከዚህ ዓለም ፍትወት መጠበቅ  እንዳለብን አሳስበለዋል፡፡ አሁንኮ እስከ ጋብቻ ድረስ በድንግልና መጽናት ከባድ ሆኖብናል፤ የ «መ» ሕጎች እየተባለ በትምህርት ቤቱ ሁሉ መከራ የሚበላው ይህን ሕግ እየረሳን ነው፡፡ ልክ የዚህን ዓለም ፍትወት መቻል በእሳት ውስጥ ማለፍ እንደሆነ፤ ፍትወት ራሱን የቻለ እሳት ነው፤ እሳት እንኳን የቀረበውን የራቀውን ይጠራል፡፡ አባቶቻችን «እሳት ይጠራል»  ይላሉ፤ እኛ የምንኖረው በዓለም ነው፡፡ ስለዚህ ለምን በኅሊናችን የፍትወት ስሜት መጣ? ለምን በዙሪያችን ኃጢአት ኖረ? ማለት አንችልም፤ ግን ወንዙን አቋርጠን ማለፍ እንችላለን፤  ራስን በንጽሕና መጠበቅም አለብን፡፡ ወንድና ሴት ራሳቸውን ከዝሙት ስሜት ጠብቀው ሲኖሩ፤ በቤተክርስቲያን በተክሊል ሲጋቡ አክሊል ይጫንላቸዋል፤ ቤተ ክርስቲያን አክሊል ላደረገችለት ሰው ደግሞ እግዚአብሔር እጥፍ ዋጋን እንደሚከፍል ቅዱሳት መጻሕፍት ላይ ተጽፏል፡፡ እነዚህ ሰዎች እድል ወይም ምድራዊ ጥቅም ሳይኖራቸው ቀርቶ አይደለም፤ ነገር ግን ምድራዊ ፍላጎታቸውን በመግታት ከራሳቸው፤ ከጓደኞቻቸውና ከአካባቢያቸው ጋር በመታገል ለነፍሳቸው መሥዋዕት ለመክፈል ስለሚሹ ነው፡፡

፭. በትዳር መጽናት

 በክርስቲያናዊ ሕይወት ውስጥ አንድ ወንድ በአንዲት ሴት፤ አንዲት ሴት በአንድ ወንድ ጸንተው ይኖራሉ፡፡ ባልና ሚስት በመቻቻል በሰላም መኖር ከቻሉ፤ ሰው የራሱን፤ የአጋሩንና የልጆቹን ጠባይ ችሎ በትዕግሥት ከኖረ፤ ሥጋ ወደሙን ተቀብሎም፤ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን  እግዚአብሔርን የሚያገለግል ከሆነ ክርስቲያን ይባላል፡፡ በምንኩስና ሳይወሰኑ ወይም በትዳር አንድ ሳይሆኑ እንዲሁ የሚኖሩ ሰዎች ክርስቲያናዊ ሕይወትን የማይሹ ሰዎች ናቸው፤ ልክ በዘመነ ሰማዕታት ጊዜ እንደነበሩ ለጊዜው ክደናል እንደሚሉት አይነት ናቸው፡፡ ፶ እና ፷ ዓመት በትዳር እየኖሩ የብር፤ የወርቅ፤ የአልማዝና ኢዩቤልዩ የሚያከብሩ ሰዎች ተመችቷቸው እንዳይመስለን፤ ብዙ የችግር ጊዜን አሳልፈው ሊሆን ይችላል፤ እግሬን በሰበረው፤ ምላሴን በቆረጠው፤ አይኔን በሰወረው፤ ብር ብዬ በጠፋው ያሉበት ጊዜም ይኖራል፤ ግን ያን ሁሉ አልፎ መጽናት ያስፈልጋል፡፡

በትዳር ያላችሁ እስከመጨረሻው እንድትጸኑ፤ንጽሕናችሁን ጠብቃችሁ በመዘምርነት የምታገለግሉ፤ በስብከት፤ ለአድባራትና ገዳማት ያላችሁን እየመጸወታችሁ ከቁርሳችሁ ቀንሳችሁ፤ ሁለት ጫማ ካላችሁ አንድ ጫማ፤ ሁለት ልብስ ካላችሁ አንዱን እየለበሳችሁ፤ እኛ ይቅርብን፤ አባቶቻችን ተርበው ከተማ ለከተማ ሲንከራተቱ አንይ ብላችሁ የምታገለግሉ፤ የምታስታርቁ አባቶች፤ የጠፉትን ፈልጋችሁ የምታመጡ፤ መናፍቃንን ተከራክራችሁ የምታሳምኑ፤ አሕዛብን ወደ ጥምቀት የምታመጡ ሰዎች ሁሉ እስከ መጨረሻው ጸንታችሁ፤ ጸንተን፤ ኑ «የአባቴ ብሩካን ዓለም ሳይፈጠር የተዘጋጀላችሁን ርስት ውረሱ» እንድንባል የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፤አሜን፡፡

የመናፍቃን ቅሠጣ በቤተክርስቲያን

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጥንታዊትና ታሪካዊት ነች፡፡ አስተምህሮዋና መሠረተ እምነቷ ከአማናዊው መምህር ኢየሱስ ክርስቶስ የተገኘ በመሆኑ አማናዊትና ርትዕት ናት፡፡ ከቤተክርስቲያን ታሪክ በቀጥታ መረዳት እንደሚቻለው ቤተክርስቲያኗ «ወርቃማ» ተብለው የሚጠሩ ዘመናትን ያሳለፈች ስትሆን በዚያው መጠን እጅግ ፈታኝ የሆኑ የመከራ ጊዜያትንም አሳልፋለች፤አሁንም እያሳለፈች ትገኛለች፡፡ በአሁኑ ጊዜ ሁሉም የራሱን እምነት በሰላም ማራመድ ሲገባው  በተቃራኒው ፀረ ኦርቶዶክስ ዘመቻ  በሁለት ግንባር በመካሔድ ላይ ይገኛል፡፡

የፀረ ክርስትናው ቡድን ውድመትና የሐሳውያን መናፍስት የቅሠጣ ዘመቻ፤በሰባክያነ ወንጌል እጥረትና በአባቶች ቸልተኝነት አብያተ ክርስቲያን እየተዘጉ ናቸው፤ምእመናንንም በነጣቂ ተኲላዎች እየተበሉ ነው፡፡ ለውጡን ተከትሎ የሚነሣ ፀረ ክርስትና ቡድን  በሚወስደው ኢ-ክርስቲያናዊ እርምጃ  ምክንያት የአምልኮተ እግዚአብሔር መፈጸሚያ የሆኑት አብያተ ክርስቲያን ሲደፈሩና ሲወድሙ፤ በአገልጋዮቿ ካህናትና በተከታዮቿ ምእመናንም ላይ እስከ ኅልፈተ ሕይወት ጉዳት ሲደርስ፤ሌላ አቅም ባይኖራትም የተከታይ አቅም እያላት «ዝም በሉ የእኔን እግር ነው የሚበላው» እንደተባለው ዐይነት ነገር የደረሰባትን ጉዳትና ችግር ሁሉ በትዕግሥት፤በአርምሞና በጽሞና  ማሳለፍ ይቻላል (ዜና ቤተክርስቲያን ርእሰ አንቀጽ፤ ጥቅምት እና ኅዳር ፳፻፲፩ ዓ.ም.)

እነዚህ ፈታኝ ወቅቶች ኢትዮጵያዊያን ሕዝባዊ ጠባይን የተላበሰ የአኗኗር ዘይቤ እንዲከተሉ ከማድረጉም በላይ የተለያዩ እምነቶች ወደ አገሪቱ እንዲገቡ መንገድን አመቻችተዋል፡፡ ቤተክርስቲያኗም ከውስጥና ከውጭ በተነሱባት ፈተናዎች ምክንያት «ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው ደቀ መዛሙርቴ አድርጓቸው» (ማቴ.፳፥፲፱ ) «ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ፤ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ» (ማር.፲፮፥፲፭)  «አባቴ እንደላከኝ እናንተንም እልካችኋለሁ» (ዮሐ.፳፥፳፩) ተብሎ በወንጌል የታዘዘውን ለዓለም ለማዳረስ በምታደርገው አገልግሎት ከላይ የተጠቀሱት ችግሮች እንቅፋት ሆነውባት አገልግሎቷን በሚፈለገው መጠን መፈጸም እንዳትችል አድርጓታል፡፡

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ደግሞ የኅብረተሰቡን ችግር ምክንያት በማድረግ የተለያዩ እምነቶች አብዛኛውን የገጠርና ጠረፋማ ኀብረተሰብ የተሳሳተ አስተምህሮን በማስተማርና በጥቅም በመደለል ፍጹም ከቤተክርስቲያኗ ሲያርቁት መመልከት የተለመደ እየሆነ መጥቷል፡፡ ለዚህም በቂ ማስረጃ የሚሆኑን ለሦስት ተከታታይ ጊዜያት የተካሄዱት የሕዝብና ቤት ቆጠራ ውጤቶች ምስክሮች ናቸው፡፡

ይህ የሌሎች ቤተ እምነት ተጽኖ የቤተክርስቲያን አገልጋዮች በቂ አለመሆንና የምእመናን የግንዛቤ ማነስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች ለሦስት ተከታታይ ወቅቶች በተካሄደው የሕዝብና ቤት ቆጠራ መሠረት ቊጥራቸው እየቀነስ መጥቷል፡፡ ይህም በአኃዝ ሲሰላ (በ፲፱፻፸፮ ዓ.ም፤60.02% በ፲፱፻፹፮ ዓ.ም፤ 50.6% እና በ፲፱፻፺፱ ዓ.ም፤43.5%) ይሆናል፡፡

በአሁኑ ጊዜ የአጽራረ ቤተክርስቲያን እንቅስቃሴ የሚገታና ምእመናንን በቤተክርስቲያን እንዲጸኑ ሊያደርግ የሚችል ሥራ መሥራት ካልተቻለ አሁንም ብዙ ምእመናንን ከቤተክርስቲያን  በረት ይልቅ ወደ ሌሎች ቤተ እምነቶች የመኮብለል እድላቸውን ሊያሰፋው እንደሚችል አያጠራጥርም፡፡ ስብከተ ወንጌል የቤተክርስቲያናችን የጀርባ አጥንት ነውና የግራኝ አሕመድ ጊዜ እንደገና እንዳያገረሽ፤ቤተክርስቲያናችን ዘመቻ ፊልጶስን ልታውጅ ይገባታል፡፡

ምንጭ፡ዐውደ ርእይ፤ ስለ ወንጌል እተጋለሁ! መጽሔት ከሰኔ ፲፬ እስከ ፲፮/፳፻፲፩ ዓ.ም.

 

የዐዋጅ አጽዋማት

በተክለሐዋርያት

የዐዋጅ አጽዋማት በቤተክርስቲያን ለምእመናን ሁሉ አሳውቆ በአንድነት የሚጾም ጾም ነው፤ በሰባትም ይከፈላል፤ እነርሱም የነቢያት  ጾም፤ ጾመ ገሃድ ወይም ጋድ፤ ጾመ ነነዌ፤ የዐብይ ጾም፤ጾመ ድኅነት፤ የሐዋርያት ጾም እና ጾመ ፍልሰታ ናቸው፡፡ በጾም ወቅት ከአንድ ምእመን የሚጠበቁ ምግባራት ደግሞ የሚከተሉት ናቸው፡፡

ሀ. ዕለት ዕለት አብዝቶ መጸለይ

በጾም ወቅት ልናዘወትራቸው ከሚገቡን ምግባራት መካከል ጸሎት አንዱ ነው፤ በጸሎት ያልታገዘ ጾም ከንቱ ነው፤ ኦርቶዶክሳዊ ምእመን በጾም ወቅትና ከጾም ወቅት ውጪ በጸሎት ትጉ መሆን ክርስቲያናዊ ግዴታው ነው፡፡ ጸሎት ከፈጣሪ የምንገኛኝበት ክርስቲያናዊ ምግባር ነው፡፡ ጸሎት ወደ ፈተና እንዳንገባ የሚረዳን የጽድቅ መሥመር ነው፡፡ ‹‹እግዚአብሔርን በጠራሁት ጊዜ ጽድቄን ሰማኝ ጭንቀቴንም አራቀልኝ ይቅር አለኝ ጸሎቴንም ሰማኝ››(መዝ.፬፥፩)

ለ. ከዝሙት መከልከል

ዝሙት ነፍስና ሥጋን ይጎዳል፤ በሰማይም በምድርም ከፍተኛ ቅጣትና ሥቃይን ያመጣል፡፡ ሴሰኝነት መልካም ስምን ያጠፋል፤ ክብርን ያሳጣል፤ ኅሊናን ይበጠብጣል፤ ከዚህ የሚከፋው ደግሞ ከእግዚአብሔር አንድነት የሚለይ መሆኑ ነው፡፡ ሴሰኞችና አመንዝራዎች ከእግዚአብሔር ዘንድ ፍርድ ይደረግባቸዋል፡፡ ነቢዩ ‹‹ወንዶችም ደግሞ ከአመንዝሮች ጋር ይጫወታሉና፥ ከጋለሞቶችም ጋር ይሠዋሉና ሴቶች ልጆቻችሁ በሰሰኑ ጊዜ፥ ሙሽሮቻችሁ በአመነዘሩ ጊዜ አልቀጣኋቸውም፤ የማያስተውልም ሕዝብ ከአመንዝራ ጋር ይቀላቀላል፡፡ (ሆሴ.፬፥፲፬)

ሐ. የስሜት ሕዋሳትን ማስገዛት

በጾም ወቅት ሁሉንም የስሜት ሕዋሳቶችን መግዛት መቻል አለብን፡፡ የስሜት ሕዋሳትን መግዛት ካልቻልን በምኞትና በፍትወት ገመድ እየጎተቱ ወደ ኃጢአት ይወስዱናል፡፡ ለዚህም ነው ሊቁ ቅዱስ ያሬድ በድጓው ይጹም ዓይን (ዓይን ይጹም) ፤ ይጹም ልሳን(አንደበት ይጹም)፤ዕዝንኒ ይጹም እምሰሚዐ ሕሱም (ጆሮም ክፉን ከመስማት ይጹም)፤ በማለት ያስተማረን ዓይን የሚያየውን ጆሮም የሚሰማውን አንደበትም የሚናገረውን ክፉ ነገር አእምሮ ወደ ሐሳብ በመቀየር ወደ ኃጢአት ሊያመራን ይችላል፡፡ በመሆኑም በጾማችን ወይም በክርስትናችን ዓይናችንን ክፉ ነገርን ከማየት አንደበታችንን ክፉን ከመናገር ጆሮአችንንም ክፉን ከመስማት ልንከለክል ይገባናል፡፡ ‹‹ኃጢአትን ወደ መውደድ አንተን ከሚስቡህ ከማየት ከመስማት ተጠበቅ›› (ማር ይስሐቅ)፡፡ ዓለሙንና በዓለም ያለውን አትውደዱ ዓለሙን የሚወድ ግን የአብ ፍቅር በእርሱ የለም በዓለም ያለው ሁሉ እርሱም የሥጋ ምኞትና የዓይን አምሮት ስለገንዘብም መመካት ከዓለም እንጂ ከአብ አይደለም፡፡ (፩ዮሐ.፪፥፲፭‐፲፮)

መ. ቅዱሳት መጻሕፍትን መመርመር ፤ መመልከት

ቅዱሳት መጻሕፍት የሰው ልጅ የፈጣሪውን የእግዚአብሔርን ሕግና ሥርዓት ይማርባቸው ዘንድ የተሰጡትና ከአለማወቅ ወደ ማወቅ ከሞትም ወደ ሕይወት የሚወስዱት የሚያደርሱት ከፈጣሪው ጋርም እንዴት መኖር እንደሚገባው የሚያስተምሩት የቅድስናው መሠረቶች የክርስትና ሕይወት መመሪያዎች ናቸው፡፡ ለዚህም ነው የእግዚአብሔር ቃል ‹‹መጻሕፍትን ካለማወቃችሁ የተነሣ ትስታላችሁ›› በማለት ያስተማረን ቅዱሳት መጻሕፍት እንዴት መጾም እንዳለብን በጾማችን ወቅት ምን ምን ተግባራትን ማድረግ እንዳለብንና እንደሌለብንም ጭምር ያስተምሩናል በጾም የተጠቀሙ የቅዱሳን አባቶቻችንንም ታሪክ እየነገሩን እኛም እንድንጾም ያደርጉናል፡፡

በመሆኑም ኦርቶዶክሳውያን  ምእመናን በጾም ወቅት እነዚህን ቅዱሳት መጻሕፍትን አብዝቶ በማንበብ ወደ ቅድስና ሕይወት የሚወስዱ የእግዚአብሔርን ሕግና ትእዛዛትን መረዳትና መፈፀም ተገቢ ነው፡፡

ሠ. ምጽዋትን ማዘውተር

ምጽዋት ማለት መስጠት፤መለገስ ማለት ነው፡፡ ይህም ከጾም ጋር ከሚተባበሩ ክርስቲያናዊ ምግባራት አንዱ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ድሆችን እናስብ ዘንድ ብቻ ለመኑን ይህንም ላደርግ ደግሞ ተጋሁ›› በማለት እንዳስተማረን ምጽዋት ለምእመናን ትጋት ናት፡፡ (ገላ.፪፥፲)

ምጽዋት መስጠት ከገንዘብ ከዕውቀት ከንብረት…ላይ ለእግዚአብሔር ቤት መለገስ ነው፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአንቀጸ ብፁዓን ትምህርቱ “ብፁዓን መሐርያን የሚምሩ ብፁዓን” ናቸው ያለውን ሊቃውንት ለምጽዋት ሰጥተው ሲተረጉሙት በሦስት መንገድ ያስቀምጡታል፡፡ እነዚህም፡-

.ምሕረት ሥጋዊ፡ ይህ የሚያስረዳው ለሥጋ የሚኾን ነገርን መለገስን ሲኾን
. ምሕረት መንፈሳዊ፡ በምክር በትምህርት ሥነ ልቡናን የሚያንጽ (የሚያበረታታ) ማድረግን ነው፡፡

. ምሕረት ነፍሳዊ፡ ደግሞ «መጥወተ ርእስ» ወይም ራስን እስከ መስጠት መድረስን ነው፡፡ (ማቴ.፭፥፯ትርጓሜ ወንጌል)

ምጽዋት ካለን ነገር ላይ ማካፈልን ያመለክታል፡፡ ለፍጹምነትም የሚያበቃ ምግባር መኾኑ የተመሰከረለት ነው፡፡ «ፍጹም እንድትኾን ለድኻ ስጥ» እንዲል (ማቴ.፲፱፥፳፩) እንደዚሁም «የሚሰጥ ብፁዕ ነው» የሚለው ኃይለ ቃል የሚያስረዳን ይህንኑ ነው፡፡ (ሐዋ.፳፥፴፭) በዕለተ ምጽአትም ከሕይወት ቃል አንዱ በምጽዋት የሚገኝ መኾኑ እሙን ነው፡፡ (ማቴ.፳፭፥፴፭) ምጽዋት በልብስ በገንዘብ እንጀራ በመቁረስ የመሳሰሉትን ለደኃ በመስጠት ለድሆችና ለጦም አዳሪዎች ማካፈል ነው፡፡ በኢየሩሳሌም የሚኖሩ ምእመናን ሀብታቸውን ለደኃ ያካፍሉ ነበር፡፡ (ሐዋ.፬፥፴፪፣፮፥፩) እንደዚሁም ዕውቀትን ማካፈል ምክር መለገስ ከምጽዋት የሚቈጠር ሲኾን ለእግዚአብሔር ቤትም በገንዘብ በጉልበትና በስጦታችን ማገልገል የምጽዋትን ዋጋ ያስገኛል (ዘዳ. ፲፭፥፲፩‐፲፭፤ኢሳ.፶፰፥፯፤፯፤ምሳ.፫፥፳፯፤ሮሜ.፲፪፥፰) እንግዲህ በጾማችን ለኃጢአታችን ሥርየትን፤ ምሕረትና ይቅርታን የምናገኝባቸውን የሥጋና የነፍስ በረከትንም የምንታደልባቸውን እነዚህን ክርስቲያናዊ ምግባራት በሕይወታችን አዘውትረን ልንፈጽማቸው ይገባናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

 

የዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተና

የተከበራችሁ አንባብያን በዘመናችን ቤተ ክርስቲያን ያለችበትን ሁኔታና በየአካባቢው እና በየክልሉ በቤተ ክርስቲያንና በክርስቲያኖች ላይ እየተፈጸመ ያለውን ጥቃት አስመልክቶ  ክፍል አንድ፤ክፍል ሁለት እና ክፍል ሦስት ጽሑፍ ማቅረባችን ይታወቃል፡፡ክፍል አራትን እነሆ ብለናል፡፡

አሁን እየተፈጸመ ያለውም አስቀድሞ ሲፈጸም ለኖረው ቀጣይ ይመስላል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ላይ እየተፈጸመ ያለውን ውድመት፤ ዜና ቤተ ክርስቲያን፡- የግራኝ አህመድ ዘመን ተመልሶ እንዳይመጣ እንዲህ በማለት አሳስቧል፡፡ «አሁን በቅርቡ ባሳለፍነው በ፳፻፲ ዓ.ም መገባደጃ ላይ አገር የሆነችውን ወይም ሁለንተናዊ ጠቀሜታዋና ትሩፋቷ ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ባለውለታ የሆነችውን አንጋፋዋን ቤተ ክርስቲያን ከሌላው ነጠሎ ለመምታትና የተከታዮቿን የምዕመናንን አሻራ ከገጸ ምድር ለማጥፋት ወይም አሳምኖ የራሱ ተከታዮች ለማድረግ የረጅም ጊዜ ዕቅድ ባለው የሱማሌ ክልል ፀረ ክርስትና ቡድን በፈጸመው ጥቃት በክልሉ ውስጥ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያንን በሙሉ አውድሟቸዋል፤ ሀብታቸውን፣ ንብረታቸውንና ቅርሶቻቸውንም ዘርፏቸዋል፤ አገልጋዮቿንም እንደ ካህኑ ዘካርያስ በየቤተ መቅደሳቸው ውስጥ አርዷቸዋል»፡፡ ይህ የሚያሳየው በቤተ ክርስቲያን ላይ እየተፈጸመ ያለው ጥፋት ጊዜያዊ ጥቃትና ተራ ጥፋት አለመሆኑን ነው፡፡ በ፳፻፱ ዓ.ም በለገጣፎ የሚገኘውን የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን የንግሥ በዓል በሚያከብሩበት ወቅት የከተማው ማዘጋጃ ቤት የላካቸው አፍራሽ ግብረ ኃይል ሰኔ ፴ ቀን በግሬደር አፍርሶታል፡፡ ሰላምን ማስፈን፣ ዜጎቹን በእኩል አይን ማየት የማገባው የሕዝብ አስተዳደር አካል ይህን ማድረጉ የሚያስገርም ነበር፡፡ በያዝነው ዓመትም በዚያው አካባቢ ቤታቸው የፈረሰባቸው ዜጋዎች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሲጠለሉ ቤተ ክርስቲያን ለምን ለችግረኞች መጠጊያ ሆነች የሚሉ ወገኖች ካህናትን ማስፈራራታቸው በመገናኛ ብዙኃን ተገልጧል፡፡

«መጋቢት ፲፫ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም በሂደቡ አቦቴ ወረዳ ኤጄሬ ከተማ የመጥምቀ መለኮት ትዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያንን ቁልፍ ሰብረው በመግባት ታቦቱንና ንዋያተ ቅድሳቱን ዘርፈው ንዋያተ ቅዱሳቱን ሹንቁራ በሚባለው ተራራ ላይ አቃጥለውታል፡፡ መጋቢት ፲፮ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም በዚሁ ወረዳ የሚገኘውን የአድዓ ቅዱስ በዓለወልድ ቤተ ክርስቲያን ቀን ላይ በእሳት አቃጥለውት ንዋያተ ቅዱሳቱ ሲቃጠል ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑ በምእመናን ርብርብ ተርፏል»፡፡ ቤተ ክርስቲያን በዚህ ሁሉ መከራ መካከል ሳትጠፋ የምትኖር ቢሆንም፣ አብረውን የሚኖሩ ወገኖቻችን እንዲህ ዓይነት የጭካኔ ተግባር የሚያሳዝንም የሚያስገርምም ነው፡፡

 ለ. የቤተ ክርስቲያን ይዞታ መነጠቅና ደን መቃጠል፣ ቤተ ክርስቲያን የዓደባባይ በዓላትን የምታከብርባቸው የመስቀል ደመራና የጥምቀት ማክበሪያ ቦታዎቿ ችግር እየገጠማቸው ነው፡፡ ከጥቂት ዓመታት ወዲህ ይዞታዋን እየነጠቁ ለባለሀብቶች መስጠት፣ ለሌለ እምነት ተቋም ማሸጋገር የተለመደ ሆኗል፡፡ በጎንደር፣ በባሕርዳር፣ በአርባምንጭ፣ እና በሌሎችም ለጥምቀተ ባሕር የሚሆኑ ቦታዎች ለባለሀብቶች ተሰጥተው በተፈጠረ ብጥብጥ ብዙ ሰው ሞቷል፤ ብዙዎች ለእስር ተዳርገዋል፡፡ የአየር ጤና ኪዳነ ምሕረት የጥምቀተ ባሕር ማክበሪያ ቦታ በወቅቱ የከተማዋ ከንቲባ በነበረው ግለሰብ ትእዛዝ ለሌላ ቤተ ዕምነት ተሰጥቷል፡፡ መንግሥት በሰጣቸው ሥልጣን እምነታቸውን የሚያስፋፉ፣ በተገኘው አጋጣሚ የቤተ ክርስቲያን የነበረውን ቦታ ሁሉ ለራሳቸው በማድረግ እንቅልፍ የሌላቸው ምእመናን ይዞታቸውን ለማስመለስ ሲነሡ ለእስር የሚዳርጉ፤ በጥይትና በዱላ እንዲደበደቡ የሚያደርጉ ወገኖች ብዙ ናቸው፡፡

 «የካቲት ፳፻፭ ዓ.ም በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊበን ዝቋላ ወረዳ አዱላላ ከተማ በሚገኘው የዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም መንሥኤው ያልታወቀ እሳት ተነሥቶ በከባድ የነፋስ ኃይል እየተገዛ ወደ ገዳሙ እንዳይስፋፋ ተሰግቶ ነበር፡፡ ገዳሙ ከዚህ በፊትም መጋቢት ፲ ቀን ፳፻፩ ዓ.ም በደረሰው የእሳት ቃጠሎ አርዘሊባኖስ፣ የሐበሻ ጥድ እና መሰል ሀገር በቀል ዛፎች ወድመዋል፡፡ መጋቢት ፰ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም በተቀሰቀሰ ቃጠሎ ገዳሙ ጉዳት ደርሶበታል፡፡» ቃጠሎውን የፈጸመው ባይታወቅም የእኛ ጥያቄ የሀገር ሀብት የሆነው ደን ሲወድም የቤተ ክርስቲያን በመባል ብቻ ትኩረት ሳይሰጠው መቅረቱ ተገቢ አለመሆኑን ለመግለጽም ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ስለሆነ ብቻ ትኲረት ሳይሰጠው መቅረቱ ተገቢ አለመሆኑን መረዳት ተገቢ ነው፡፡ በአንድ አካባቢ በቤተ ክርስቲያን ላይ ችግር ሲፈጠር በወቅቱ መረጃው እንዳይወጣ ይደረግ የነበረው ጫና ቀላል አልነበረም፡፡

ምእመናን የተናገሩትን፣ መነኮሳት የተሰማቸውን አካቶ ዜና ለመሥራት የነበረው ችግር ቀላል አልነበረም፡፡ ሀገራችን ዘመናዊ የእሳት ማጥፊያ እንደሌላት ይታወቃል፡፡ በሚችሉት መርዳት፣ በአሳብ መደገፍ፣ ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶ በምንችለው ሁሉ ተረባርበን እናጠፋለን፡፡ ይህ የቤተ ክርስቲያንና የሀገር ሀብት የሆነው ቋሚ ቅርስ ለጉዳት ሲጋለጥ ሃይማኖት ዘርና ቀለም ሳንለይ ችላ አላልንም በማለት የባለቤትነት ስሜት እንዳን ሁላችንም ማሳወቅ ይኖርብናል፡፡ ይህ ጉዳት በታላቁና በጥንታዊው የአሰቦት ደብረ ወገግ ሥላሴ ገዳምም ተፈጽሟል፡፡ የገዳሙን ደን አክራሪዎች ባስነሡት እሳት መቃጠሉ በወቅቱ ተዘግቧል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ላይ፣ ችግር ሲፈጠር ከክርስቲያኖቹ ያላነሰ ልባቸው የሚያዝን፣ አቅማቸው የፈቀደውን ሁሉ የሚያደርጉ የሌላ ከክርስትና ውጪ ያሉ ዕምነት ተከታዮት እንዳሉ አንክድም፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ማየት የማይፈልጉ በሐሰት መረጃ የተሞሉ ጥፋት አድራሾችም እንደዚሁ፡፡ እየተፈጸመ ያለው ጥፋት በንፁህ ኅሊና መለስ ብለን ማየት ካልቻልን፣ ትኩረት አለመስጠታችንና ጆሮ ዳባ ለበስ ማለታችን የበለጠ ጥፋት ያስከትላል፡፡

ከታሪክ ምሁራን፣ ከቤተ ክርስቲያን፣ ከመገናኛ ብዙኀንና ከመንግሥት አካላት ስለ ቤተ ክርስቲያን በስሕተት ሲዘራ የኖረውን ታሪክ ማስተካከልና ትክክለኛውን መረጃ መስጠት ያስፈልጋል፡፡ ለምን ገዳማት በዙ፣ ለምን ቱሪስቶችን የሚስቡት የክርስቲያኖች የተጋድሎ ውጤቶች ሆኑ የሚሉ ወገኖች በቅናት ታሪክ ለመቀየር እየሠሩ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ምሁራን ለሚጻፉ የሐሰት ጽሑፎች መልስ መስጠት፣ የመረጃቸውን ፍሬ ቢስነት ማጋለጥ ይኖርባቸዋል፡፡ እንደፈለጋቸው ሲሳደቡ ቤተ ክርስቲያን ከዛሬ ነገ ይታረማሉ በማለት በትዕግሥተ ስላለፈችው፡፡ ስታልፈው በጥሞና የራስን ምግባር ማየት ይገባል እንጂ በጥፋት ላይ ጥፋት መፈፀም ሰብዓዊነት አይደለም፡፡ ይህ መሰተካከል ይኖርበታል፡፡ የራሳቸው እምነት ተከታይ ሆነው ሚዛናዊ ጽሑፍ ያቀረቡትን የሚያጣጥሉ፣ ምንጭ የሌለው የጥላቻ ጽሑፍ የሚጽፉትን ታላቅ ነገር እንዳገኙ ሁሉ እየጠቀሱ ሲያሞካሹ ሕሊናቸውን እይቆጠቁጠውም፡፡ ኦርቶዶክሳውያንም ብቻ ሳይሆኑ ሌሎች ምሁራንም ምርቱን ከገለባው፣ እውነቱን ከሐሰት በመለየት ለአንባብያን ማድረስ አለባቸው፡፡

በየጊዜው እነዚህ ጥፋቶች ተፈፀሙ ስንል፣ በጥፋቱ ላይ የተሠማሩ ሰዎች ወደ ኅሊናቸው እንዲመለሱ እንጂ እሳትን በእሳት አጥፉ ለማለት አይደለም፡፡ በቤተ ክርስቲያን ላይ በዚህ አምሳ ዓመት የተፈጸመው በዓላማ መሆኑን የሚያሳየው በአንድ ወቅት በሀገሪቱ ከፍተኛ የሥልጣን ርከን ላይ የነበሩ ሰው «ሥልጣኑን ከአማራና ከኦርቶዶክስ አርቀነዋል» በማለት ጠቅላይ ሚኒስቴር ኃይለ ማርያም የተመረጡ ሰሞን መናገራቸው ማሳያ ነው፡፡ እንደዚያ ማለት መብታቸው ቢሆንም፣ በመንግሥት ኃላፊነት ላይ ሆኖ ለሀገር ባለውለታ የሆነችን፣ ቅርሶቿ በዓለም የምርምር መድረክ ግንባር ቀደም ሚና የምትጫወትን ቤተ ክርስቲያን ማጥፋት ወይም አጥፊዎች ሲያወድሟት ቆሞ ማየት ተገቢ ነው ብለን አናምንም፡፡ በመሆኑም እንዲህ ዓይነት ሰዎችና አካላት ቤተ ክርስቲያን ለማጥፋት ብለው ሲሠሩ ኦርቶዶክሳውያን እና የሚያመዛዝኑ ወገኖች ደግሞ ቢችሉ በመገሠጽና በማረም ቢይችሉ የጥፋት ተባባሪ ባለመሆን የቤተ ክርስቲያን እና የሀገር ሀብት እንዳይጠፋ ማስጠበቅ ይኖርባቸዋል፡፡ በህዝብ አስተዳደር ላይ የሚገኙ አካላትም በታሪክ ላለመጠየቅ ከሕሊና ፍርድም ነፃ ለመሆን ቤተ ክርስቲያን ሲቃጠል ምእመናን ሲሳደዱና ሲገደሉ ሕጋዊ ርምጃ መውሰድ ይኖርባቸዋል፡፡ የራሳቸው በሆነ ስሜት ውስጥ ሆነው የሚነጐዱ ሰዎች ለከፋና ዕውነታውን ከመቀበል ይልቅ፣ ለበለጠ ነገር በእልክ መሔድን የሚመረጡ ስለሆነ ‹‹ጨርሰን ባንበገር›› ቢቀር?

 ማንኛውም የዕምነት ተቋም ተከታዮች ሲሞቱ የሚያሳርፍበት ቦታ ሕጋዊ በሆነ መንገድ ጠይቆ ማግኘት መብቱ ቢሆንም፤ በሲዳሣ ሀገረ ስብከት የወንዶ ገነት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያንን የቀብር ቦታ ፕሮቴስታንቶች ሕገ ወጥ በሆነ መንገድ ወስደው የራሳቸው የቀብር ቦታ አድርገውታል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ይዞታዋን ለማስመለስ እስከ ሰበር ሰሚ ችሎት ተከራክራ ይዞታዋ ቢወሰንላትም የፍርድ ቤቱን ውሳኔ የሚያስተገብር በመጥፋቱ ጉዳዩ ወደ ፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ተሸጋግሮ ይገኛል፡፡ በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ለቤተ ክርስቲያን መሥሪያ ቦታ ሲጠየቅ በጎ ምላሽ አለመገኘቱ የልማት ቦታም በሊዝ ካልሆነ ማግኘት አለመቻሉ ተገልጧል፡፡»ክርስቲያኖችም ከስሜታዊነት ወጥተን በማስተዋል እንመላለስ፡፡ አካባቢያችንንም እንጠበቀ፣ ለመንግሥት አካላትም ትክክለኛውን መረጃ እናድርስ፡፡ የሚፈጸሙ ጥፋቶች እንዲቆሙ ድምፃችንን እናሰማ ጥፋቶችንም መዝግበን እንያዝ፡፡

ይቆየን

ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ከሰኔ ፩-፲፭ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም

የዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተና

 

የተከበራችሁ አንባብያን በዘመናችን ቤተ ክርስቲያን ያለችበትን ሁኔታና በየአካባቢው እና በየክልሉ በቤተ ክርስቲያንና በክርስቲያኖች ላይ እየተፈጸመ ያለውን ጥቃት አስመልክቶ ክፍል አንድና ሁለትን  ጽሑፍ ማቅረባችን ይታወቃል፡ ፡ከፍል ሦስት እነሆ ብለናል፡፡

ቤተ ክርስቲያንን ለማጥፋት የተነሡ አካላት ለጥፋታቸው የሚጠቅሱትን የፈጠራ ታሪክ ቤተ ክርስቲያን ከክርስቶስ ልደት እስከ አሁን ያበረከተችውን አስተዋጽኦ በመጠኑ አሳይተናል፡፡ የገጠማትን ፈተና፣ ሊወጓት የመጡትን ያለዘበችበትን መንፈሳዊ ጥበብ ባለፈው ዝግጅት አቅርበናል፡፡ በተለይ ከ፲፱፻፹፫ ዓ.ም ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን ላይ እየደረሰ ያለውን ጥፋትና የመንግሥት አካላትን ምላሽ ፍርድ ቤትን ጨምሮ ማቅረብ ጀምረናል፡፡ ባለፈው የጀመርነውን ቤተ ክርስቲያንን የማቃጠል ጥፋት መረጃዎችን በመጨመር ወደ ቀጣዩ እናልፋለን፡፡

በየቦታው ቤተ ክርስቲያን ትቃጠላለች፡፡ መቃጠሉ በዓላማ መሆኑ የሚታወቀው አሻራው እንዳይገኝ ወዲያውኑ የሌላ ዕምነት ቤት፣ የሌላ ዕምነት ቤት አዳራሽና ሌላም እንዲሠራበት መደረጉ ነው፡፡ «በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ቤተ ክርስቲያኖች ተቃጥለው ወደ መስጊድነት የተቀየሩ መሆናቸውን የአካባቢው ምዕመናን ይህ እኮ ቤተ ክርስቲያን የነበረበት ነው» እያሉ ቦታውን የሚያመለክቱት በቁጭት ነው፡፡ የሚፈጸመው ጥፋት የራስን ዓላማ ለማሳካት የሌላውን መብት መጋፋት ትክክለኛ ተደርጐ ሲፈጸም እየታየ መሆኑን መረዳት ይገባል፡፡ ዓላማን ማሳካት አንድ ነገር ነው፡፡ የሌላውን መብት እየተጋፉ ዓላማን ማሳካት ግን ተገቢነት የሌለው ነው፡፡ የሌላውን ተደራጅቶ ማጥፋት በጥንታዊት ማሌ፣ በሴኔጋል፣ በጥንታዊት ግብፅና ሜርዋ፣ በርበሮችና አክራሪዎች ነባር የሥልጣኔ አሻራዎችን ማጥፋታቸውን አስታውሰን ነቅተን እንድንጠብቅ ያደርገናል፡፡ ነባሮቹና ተረጋግተው በመኖር ላይ የሚገኙ ሙስሊሞች በዕምነታቸው ስም ተገቢ ያልሆኑ ተግባራትን የሚፈፅሙ ወገኖቻቸውን ማስታገስ ይኖርባቸዋል፡፡ መንግሥትም ምንም እንዳልተፈጠረ አድርጐ ሳይመለከት ሌሎችን የሚያስተምር ርምጃ መውሰድ ይኖርበታል፡፡

በዚህ ሀገር እስላሙም፣ ክርስቲያኑም፣ ፕሮቴስታንቱም የመኖር መብት አለው፡፡ አንዱ ገፊ ሌላው ተገፊ፣ አንዱ ባለ አገር ሌላው አገር የሌለው መምሰል የለበትም፡፡ ይህ ሃይማኖት የእነ እገሌ ነው ያንተ ሃይማኖት ይህ ነው ማለትም ፖለቲካ እንጂ ሃይማኖት አይደለም፡፡ ሃይማኖት የሚሰበከው የሃይማኖት ትምህርት ባላቸው ወገኖች እንጂ፣ የፖለቲካ ዓላማ ባላቸው  የጥፋት ኃይሎች አይደለም፡፡ የምናመልከውን በሚመርጡልን ወገኖች ሃይማኖተኛ መሆን የለብንም፡፡ ሰሞኑን በሊሙ ኮሳ በዕምነታቸው ሽፋን አክራሪነትን የሚያራምዱ ሰዎችና ቡድኖች ክርስቲያኖችን ከማጥፋት አልፈው ‹‹ክርስትና የአማራ ነው የኦሮሞ ክርስቲያን የለውም›› በማለት ይቀሰቅሱ እንደነበር ተሰምቷል፡፡ የኦሮሞ ክርስቲያን እንዳይኖር ከክርስትና ውጪ ሌሎች የኦሮሞ ሃይማኖት እንዲኖር የፈቀደው ማን ነው? አክራሪነት ሥሩ የት ሆኖ ነው የኦሮሞ ሃይማኖት መስሎ የሚሰበከው፡፡ ይህ አብረን እንዳንኖር የሚያደርግ ተባብሮ ለማጥፋት የተደረገ ሴራ መሆኑን መረዳት ይገባል፡፡ የሚያምነው ሃይማኖት መምረጥ ያለበት ራሱ ምእመኑ እንጂ በኋላቸው ፖለቲካ አንግበው የግል ጥቅማቸውን የሚያሳድዱ ወገኖች መሆን የለባቸውም፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ይህን የሚለው ሰላም የሚገኘው ሰላማውያንን በመግፋት ባለመሆኑ የበለጠ ጥፋት እንዳይፈጠር ነው፡፡ ይህ የእኔ ነው አትድረሱብኝ ማለትና ነባር ገዳማት ያለባቸውን ሁሉ ይጥፉ ማለት ሰላም አያመጣም፡፡

በጀጁ ወረዳ አቦምሳ ቅዱስ እግዚአብሔር አብ፣ አቡሌ ቅዱስ ጊዮርጊስ፣ አብሸራ መድኃኔዓለም በጉና ወረዳ አንድሬ ቅዱስ ጊዮርጊስ፣ ተራም ቅዱስ ገብርኤልና መሶ ቅዱስ ገብርኤል አብያተ ክርስቲያናት ሙሉ በሙሉ በእሳት ሲወድሙ ሁለት አብያተ ክርስቲያናት ፈርሰው፣ ጽላቱን ጨምሮ ሌሎች ንዋያተ ቅድሳት መዘረፋቸው ከዓመታት በፊት ተዘግቧል፡፡ ይህን የምናቀርበው መንግሥት ባለበት ሀገር እንዲህ ዓይነት ጥፋት መፈጸሙን በማሳሰብ ዳግም እንዳይፈጸም እንዲከላከል ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን በክርስቶስ የተመሠረተች ዘለዓለማዊት እንደሆነች ብናምንም በጥፋታችን እግዚአብሔር እንዳይቀጣን፣ ከኃጢዓት እንድንርቅ፣ እንደ ዘመነ ሰማዕታት አጥፊዎችን የሚማርክ ክርስትና የሚነበብ ክርስትና እንዲኖረን ጭምር ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያን በሰማይ አለች፣ በምድርም ትኖራለች፣ በገሀድ የሚኖሩትና የተሰወሩት አንደነት መሆኗን እየመሰከርን እኛ ግን በስንፍናችን እንዳንቀጣ መንቃት ይኖርብናል፡፡ ቤተ ክርስቲያን እንደማትጠፋ መረዳትና በእምነት መጽናት ይኖርብናል፡፡ ዲያብሎስ ዓላማየን ያሳኩልኛል ያላቸውን አካላት ጦር እያስመዘዘ፣ ገጀራ እያስጨበጠ፣ እሳት እያስለኮሰ፣ ቃታ እያሳበ ጥፋታቸውን ጽድቅ አስመስሎ እያሳያቸው በማጥፋት ለመርካት ቢፈልጉም ደስታን እንደማያገኟት መረዳት ይገባል፡፡ ከአጥፊዎች ወገንም የዲያብሎስን ሽንገላ አልፈው የእግዚአብሔር ጥሪ ደርሷቸው የሚመጡ እንዳሉ ግልጽ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ «ሰውን ብትታገለው ያሸንፍሀል ወይም ታሸንፈዋለህ፤ ቤተ ክርስቲያን ሁል ጊዜ ትዋጋለች፤ ተሸንፋ ግን አታውቅም፡፡ ዲያብሎስ ቤተ ክርስቲያንን ለመውጋት ዝናሩን አራገፈ፤ ቀስቱንም ጨረሰ፤ ቤተ ክርስቲያንን ግን አልጐዳትም» በማለት ያስተማረውን ክርስቲያኖች በተግባር ተፈጽሞ፣ ያዩት ነው፡፡ ይህንን እያመንንም ቤተ ክርስቲያን ሲቃጠልና ምእመናን ቦታችሁ አይደለም ተብለው ሀብት ያፈሩበትን፣ ወልደው ከብደው የኖሩበትን ቦታ ሲለቁ ችግሩ እየተባባሰ ሔዶ ልንቋቋመው ከማንችልበት ደረጃ እንዳይደርስ እንደ እባብ ልባሞች እንደ ርግብ የዋሆች በመሆን ማሰብ አለብን፡፡ የግል ፍላጐታቸውንና ዓላማቸውን ለማስፈጸም ሀገራችንን በተፅዕኖአቸው ሥር ማድረግ የሚናፍቁ ወገኖች እርስ በርስ ስንፋጅ ዓላማቸውን እንዳያስፈጽሙብን፣ መሬታችንን እንጂ እኛን ስለማይፈልጉ የሩቅ ተመልካች ሆነው ሰንጫረስ ቆመው አይተው ሀገራችንን እንዳይወሰዱብን ጭምር ነው፡፡

በሥልጣኔ ሰበብ፣ በሉላዊነት ስም እየተፈጸመ ያለውን ድሀ ሀገሮችን የማዳከምና በጠንካራው የመዋጥ መጥፎ አካሔድ እንዳይደርስብን ዘመኑን የሚዋጅ ተግባር መፈጸም ግድ ይላል፡፡ በጦርነት አልሳካ ያላቸውን በማዘናጋትና በተናጥል በሚፈጽሙት ጥፋት ከእስከ አሁኑ የበለጠ እንዳንጐዳ እየተፈጸመ ያለውን እኩይ ተግባር መረዳት ይገባል፡፡ በሌሎች ሀገራት ከተፈጸሙ የሀገርን ቅርስ አጥፍቶ በአዲስ የመተካት ድርጊት ልንማርበት ይገባል፡፡ ቤተ ክርስቲያንን የሚያቃጥሉ፣ ምእመናንን የሚያሳድዱ፣ ይዞታዋን የሚቀሙ ወገኖች በአፅራረ ቤተ ክርስቲያን ቤተ ክርስቲያንንና ሀገራቸውን የሚያስጠላ ትምህርት ሲጋቱ የነበሩ ናቸው፡፡ በዚህም የምዕራባውያን አድናቂዎች፣ የራሳቸውን ግን አናናቂዎች ሆነዋል፡፡ የጻፏቸውን የጥላቻ መጻሕፍት እየጠቀሱ ቤተ ክርስቲያንን ሲያብጠለጥሏት ኖረዋል፡፡ እነዚህ ወገኖች ሥልጣን ሲይዙም ቤተ ክርስቲያንን ለሀገሪቱ ኋላ መቅረት አስተዋጽኦ ያደረገች አስመስለው ከመሳል አልፈው በክርስቲያኖች ላይም ጥላቻና ጥርጣሬ አሳድረዋል፡፡ ይህን ጉዳይ ዮሐንስ አድገህ የተባሉ ተመሪማሪ «ከዚያ በኋላ (ከንጉሡ ቀጠሎ) የመጣው መንግሥትም ዓላማዊነት (secularism) በሚል ከንቱ ፍልስፍና ተጀቡኖ ለሃይማኖት ቦታ የማይሰጥ፣ ይልቁንም ቤተ ክርስቲያኒቱን የነገሥታት መጨቆኛ መሣሪያ እንደነበረች አድርጐ በመሳል በሕዝብ ዘንድ ያላትን ተቀባይነት ለመቀነስ ይሞክር ነበር» ብለዋል፡፡

ይቆየን

ምንጭ ፤ ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ከሰኔ!  ፩ -፲፭ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም

 

ዕረፍት ያጣች ነፍስ!

በሕይወት ሳልለው

እግዚአብሔር አምላካችን በአርአያውና በአምሳሉ ሲፈጥረን በክብር ነውና ከአለመኖር ወደ መኖር ያመጣንም በእስትንፋሱ ነበር፡፡ «እግዚአብሔር አምላክም ሰውን ከምድር አፈር ፈጠረው፤ በአፍንጫውም የሕይወት እስትንፋስን እፍ አለበት፤ሰውም ሕያው ነፍስ ያለው ሆነ»፤ (ዘፍ ፪፥፯)፤

አባታችን አዳም ባደረገው ስሕተት ከገነት ተባሮ ወደ ምድር ከወረደ በኋላ ኑሮው የከፋ ነበር፤ ብዙም ተፈትኗል፤ ገነት ሳለ ደስታን እንጂ መከራን አላወቀም፤ ነገር ግን እዚህ ምድር ላይ በፍርሃትና በጭንቀት ይኖር ነበር፡፡ ከልብሰ ብርሃንም ተራቆተ፤ ተበረደ፤ የበለስ ቅጠል ቆርጦም ለበሰ፤ በመከራውም ጊዜ የፈጣሪውን ትእዛዝ በመተላለፉ የሠራውን ኃጢአቱን በማሰብ ያለማቋረጥ ያለቅስ ነበር፡፡ ከብዙ ዘመናት በኋላም በተገባለት ቃልኪዳን መሠረት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከልጅ ልጁ ተወልዶ እስኪያድነው ድረስ በምድር ብዙ ተሠቃይቷል፡፡

ሰው ድኅነትን የሚያገኘው በክርስትና ሕይወቱ ውስጥ ለእምነትና ለሃይማኖቱ መሥዋዕትነት በመክፈል፤ ዘወትር በክርስቲያናዊ ሥርዓት፤ በምስጋናና በሕገ እግዚአብሔር ሲኖር ነው፡፡ ነገር ግን ዓለማችን በአሁኑ ጊዜ በኃጢአት ማዕበል ውስጥ ተዘፍቃለች፤ መከራ፤ ሥቃይ፤ ችግር፤ እንዲሁም ጦርነት በየሀገሩ በዝቷል፡፡ ትንቢቱም እንደሚገልጸው «ሕዝብ በሕዝብ ላይ፤ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣሉ፤ በየሀገሩም ረኃብ፤ ቸነፈርም፤ የምድር መናወጥም ይሆናል፤ እነዚህም ሁሉ የምጥ ጣር መጀመሪያ ናቸው፡፡ ያንጊዜም ለመከራ አሳልፈው ይሰጡአችኋል፤ ይገድሉአችኋልም፤ ስለ ስሜም በሰዎች ሁሉ ዘንድ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ፡፡ ያን ጊዜም ብዙዎች ሃይማኖታቸውን ይለውጣሉ፤ እርስ በእርሳቸውም አሳልፈው ይሰጣጣሉ፤ እርስ በእርሳቸውም ይጣላሉ» (ማቴ. ፳፬፥፯-፲)፡፡

በዚህች ምድር ላይ ስንኖር ልንፈተን እንችላለን፤ በዕለት ክንዋኔያችን ውስጥ ብዙ ውጣ ውረድ ሊገጥመን ይችላል፡፡ ከጥንት ጀምሮ አእምሮአችንን ለመቆጣጠርና ትዕግስትን አስጨርሶ ተስፋ ለማስቆረጥ የሚፈታተነን ጠላት ዲያብሎስ የማሳቻ መንገዱ ብዙ ነውና በእምነት ጸንተን ልንኖር ይገባል፡፡ ተስፋ የቆረጠ ሰው ለውድቀትና ለጥፋት የቀረበ ይሆናል፤ ዕረፍትን የሚሻ ሰው ግን በተስፋ ውስጥ ለእያንዳንዱ ችግር መፍትሔ እንዳለው፤ ለእያንዳንዱ ለተቆለፈ መዝጊያ አንድ ወይም ብዙ ቁልፎች እንዳሉትና ለእያንዳንዱ ውድቀትም መነሻ እንዳለው ይታወቃል::

ሰላምና ፍቅር ከእኛ ሲርቅ ማንነታችንን መጥላት፤ የእኛ ያልሆነውን ባዕድ ጠባይ መቀበል እንጀምራለን፤ ነፍስ ግን ሁሌም ፈጣሪዋን ትፈልጋለች፤ እናም ትጨነቃለች፡፡

ዛሬም ያለው ትውልድ ከነፍሱ ይልቅ ለምድራዊ ሕይወቱ ይለፋል፤ ነገር ግን ከንቱ ልፋት ነው፡፡ «ከፀሐይ በታች የተሠራውን ሥራ ሁሉ አየሁ፤ እነሆም፥ ሁሉ ከንቱ ነው፥ነፋስንም እንደመከተል ነው»መጽሐፈ መክብብ ፩፥፲፬፡፡የሰው ልጅ ኅሊናውን ሳይክድ ለእምነቱ ተገዝቶ ሲኖር ወደ ፈጣሪው መቅረብ ይቻለዋል፤ ሁል ጊዜም አምላኩን ሲያስብ፤ በተስፋም ሲኖር፤ ወደ ክብር ቦታው እንደሚመለስ በማመን በጎ ሥራን አዘውትሮ ይተገብራል፡፡ ፈሪሀ እግዚአብሔር ያለው ሰው ፈጣሪውን ያስባል፤ ይፈራል፤ ያከብራል እንዲሁም በሕጉ ይመራል፤ ከራሱም አልፎ ለሌሎች ጥሩ ማድረግን ይመኛል፤ ያደርጋልም፡፡

እርግጥ ነው ጠባያችን እንደመልካችን ይለያያል፤ እግዚአብሔር አምላካችን በቃሉ «ብዙ ተባዙ፤ ምድርንም ሙሉአት» እንዳለው (ዘፍ. ፩፥፮)፤ በዓለማችን በቢሊዮን የምንቆጠር ሰዎች አለን፡፡ እናም ተከባብሮ የመኖር ውዴታና ግዴታ የእኛ ቢሆንም ኃላፊነትን ከመወጣት ይልቅ ክፋት፤ ተንኮል፤ በደል፤ ጥላቻ፤ ግድያ ከዛም አልፎ  ባዕድ አምላኪም በዝቷል፡፡ ፈውስና በረከት ማጣት፤ በምሬትና በሰቆቃ ውስጥ ለመኖር መንስኤው የኃጢአት መብዛት ነው፤ ክፉውም ሆነ ደጉ የሥራችን ውጤት ነው፡፡

በዚህ ምድር ስንኖር ሥጋችንንም ዋጋ በማሳጣት ለነፍሳችን ልንኖርላት እንደሚገባ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወንጌል አስተምሮናል፤ «ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢገዛ፤ ነፍሱንም ቢያጣ፤ ለሰው ምን ይረባዋል? ሰውስ ለነፍሱ ቤዛ ምን በሰጠ ነበር?» (ማቴ. ፲፮፥፳፮)፡፡

ሰላም ፍቅር ማጣት

የባዶነት ስሜት

ማንነትን መጥላት

በምሬት አንደበት

ክፉ ነገር ማውጣት

ርኩሰት በኃጢአት

ነፃነትን መሻት

  ነፍስ ስታጣ ዕረፍት

የተጨነቀች ዕለት

«እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ ወደ እኔ ኑ፤ እኔም አሳርፋችኋለሁ፤» (ማቴ.፲፩፥፳፰) ይለናልና ፈጣሪያችንን አብዝተን እንለምነው፤ እንጸልይ እንጹም፤ ዕረፍት ያጣች ነፍሳችንን እናሳርፋት፡፡

በዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተና

የተከበራችሁ አንባብያን በዘመናችን ቤተ ክርስቲያን ያለችበትን ሁኔታና በየአካባቢው እና በየክልሉ በቤተ ክርስቲያንና በክርስቲያኖች ላይ እየተፈጸመ ያለውን ጥቃት አስመልክቶ ክፍል አንድን  ማቅረባችን ይታወቃል ክፍል ሁለትን እነሆ ብለናል፡፡

ምዕራባውያንና የእነሱ ጉዳይ አስፈጻሚዎች ቤተ ክርስቲያንን ለማዳከም ይጠቅመናል ብለው ያሰቡትን ሁሉ ፈጽመዋል፡፡ የአሳባቸው አቀንቃኝ ኢትዮጵያዊ “ፈረንጆችንም” አግኝተዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንንም ሊቃውንቷንም ለመተቸት ያለ ስማቸው ስም ያለ ግብራቸው ግብር በመስጠት ጥላቻውን በመግለጽ አልሜዳ የተባለ ሚሲዮናዊ የፈጠራ ታሪክ ጽፏል፡፡ የእሱን ጥላቻ እየጠቀሱ ቤተ ክርስቲያንን የሚተቹት የግብር ልጆቹ ናቸው፡፡ የእሱን ጥፋት ዳንኤል ክብረት «አልሜዳ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን አምርሮ የሚጠላ ኋላ ቀርና በኑፋቄ የተሞላች አድርጎ የሚፈርጅ ኢየሱሳዊ /ሚስዮናዊ/ ነበር፡፡ በጽሑፎቹ ላይ ይህን ነው ሲያንጸባርቅ የኖረው፡፡ ከዚህ ጠባዩ አንጻርም አቡነ ተክለ ሃይማኖትን ቢተች የሚጠበቅ እንጂ የሚገርም አይደለም» (ዳንኤል፣ ፳፻፲፩፣፫‐፬) በማለት ገልጦታል፡፡ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌም ሆነ ተሐድሶአውያን አቡነ ተክለ ሃይማኖትን የሚተቹት የእሱን አሳብ እየጠቀሱ ነው፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖትን መንቀፍና ያለ ግብራቸው ግብር መስጠት ቤተ ክርስቲያንን ለማዳከም ይጠቅመናል ብለው ያስባሉ፡፡ ለኋለኞቹ የቤተ ክርስቲያን ተችዎች ጀማሪና ፊታውራሪያቸው አልሜዳ ነው፡፡ የውጭ ጸሐፊዎች የኢትዮጵያውያንን አእምሮ በመበረዝ ቤተ ክርስቲያን ላይ ትችት እንዲያዘንቡ ምክንያት መሆናቸውን ከአልሜዳ ጽሑፍ መረዳት ይቻላል፡፡ ለመነሻ ያህል ይህን ካቀረብን በየዘርፉ የደረሱትን ችግሮች እንደሚከተለው እናቀርባለን፡፡

ሀ. የቤተ ክርስቲያን መቃጠል፡- በየዘመናቱ፣ በየቦታው አብያተ ክርስቲያናት በአክራሪ ሙስሊሞች፣ በግለኝነት በታወሩ የፕሮቴስታንት እምነት ተከታዮችና በአጽራረ ቤተ ክርስቲያን ሲቃጠሉ ቆይተዋል፡፡ ይህን የሚያደርጉት የግል ጥላቻና የተለየ ፍላጎት ያላቸው ግለሰቦች ወይም ቡድኖች እንጂ ሁሉም የሌሎች እምነቶች ተከታዮች እንዳልሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ስትቃጠል አብረው የሚያዝኑና የሚያለቅሱ፣ ክርስቲያኖች ሲሳደዱና መከራ ሲደርስባቸው በቤታቸው የሚሸሽጉ ብሎም አብረው መከራ የሚቀበሉ፣ ክርስቲያኖች ኃይላቸውን እያሰባሰቡ አቅማቸውን እያጠናከሩ መልሰው ለመገንባት ሲደክሙ ከገንዘብ እስከ አሳብ ድጋፍ የሚያደርጉ የሌላ እምነት ተከታዮች አሁንም በየቦታው መኖራቸው የሚካድ አይደለም፡፡ በዘመናችንም ክርስቲያኖች በጥብዐት መከራውን ተቋቁመው ክርስትና በሞት፣ በስድት፣ በእሳትና በመከራ የማይፈታ መሆኑን አስመስክረዋል፡፡ በዚሁ አንጻር ግን በመገናኛ ብዙኃን በተለያዩ ቦታዎች የሚቃጠሉትን አብያተ ክርስቲያናት ያልታወቁ ግለሰቦች ያቃጠሏቸው እንደሆነ ቢነገርም ታስቦበት፣ ተጠንቶ፣ ምን ለማግኘትና ምን መልስ ለመስጠት አስቀድሞ እየታሰበ ቃጠሎው መፈጸሙን የሚጠቁሙ ማሳያዎች አሉ፡፡ ፲፱፻፺፫ዓ.ም ሚያዝያ ፲፪ ቀን በአርሲ ሀገረ ስብከት ኮፈሌ ወረዳ ጉች ቀበሌ ገበሬ ማኅበር የሚገኘው የመድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን በአክራሪ እስላሞች ለመቃጠል የቻለው ከተማ ላይ ሊያደርሱት የነበረው አደጋ በመከላከያ ሠሪዊትና በፖሊስ ስለተደናቀፈባቸው ነው፡፡ ገጠር በመግባት የክርስቲያኖችን ቤት እየመረጡ ማቃጠላቸው የታቀደና የተደራጀ ጥቃት መሆኑን ለመረዳት ይቻላል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ሃይማኖታዊ ትንኮሳ ከትላንት እስከ ዛሬ መቀጠሉ ታስቦበት እየተሠራ መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡ ይህ ድርጊት በአንድ በኩል አጥፊዎች ልብ እንዲገዙ፣ በሌላ በኩል ደግሞ መንግሥት ከትላንት እስከ ዛሬ እየደረሰ ያለውን ጥፋት በመረዳት ለእምነት ቤቶችና ለክርስቲያኖች ልዩ ጥበቃ እንዲያደርግ ሊያነቁ፣ ምእመናንም ራሳቸውን እንዲጠብቁ፣ እንዲደራጁና አዲስ ነገር ሲገጥማቸው ለፍትሕ አካላት እንዲያቀርቡ ትምህርት ሊሆን ይገባል፡፡ ክርስቲያኖች የሚማሩት ከመከራ፣ ቅድስናቸው የሚገለጠው በፈተና መሆኑ የተጻፈ፣ ክርስቲያኖች በተግባር ፈጽመው ያሳዩት ሕይወት ነው፡፡

በጅማ ሀገረ ስብከት ከመስከረም ፲፮ እስከ ጥቅምት ፬ ቀን ፲፱፻፺፱ ዓ.ም ጨጉ ቅዱስ ገብርኤል፣ ቦሬ ቅዱስ ገብርኤልና በሻሻ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አብያተ ክርስቲያናት በአክራሪ እስላሞች ተቃጥለዋል፡፡ ንዋያተ ቅድሳት ተዘርፈዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በጅማ፣ በምዕራብ በወለጋና በኢሉባቡር ከ፲፫ በላይ አብያተ ክርስቲያን ንዋያተ ቅድሳት ተዘርፈዋል፡፡ ኅዳር ፮ ቀን ፲፱፻፺፰ዓ.ም በአርሲ ሀገረ ስብከት በኮፈሌ ወረዳ የምትገኘው የአይሻ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ፀረ ክርስትና አቋም ባለው ቡድን ተቃጥላለች፡፡ አገልጋይ ካህናት በቤተ መቅደስ ውስጥ ታርደዋል፣ አሥር ክርስቲያኖች በገጀራ ተገድለው፣ አብያተ ክርስቲያናትና የክርስቲያኖች መኖሪያ ቤቶች ተቃጥለዋል፡፡ ብዙ ንብረት ወድሟል፤ ነዋሪዎች ከቀያቸው ተፈናቅለዋል፡፡ ይህ የሚያሳየው በሀገራችን ሰላም እንዳይሰፍን ሆን ብለው ግጭት የሚፈጥሩ አካላት መኖራቸውን ነው፡፡

በወቅቱ አጥፊዎችን ሊያስተምር የሚችል እርምጃ መወሰድ ሲገባ ጉዳዩ ለሕዝብ ይፋ እንዳይሆን ከመንግሥት አካላት ተጽዕኖ ይደረግ ነበር፡፡ አጥፊዎችን ማስታገስ ሲገባ ጉዳት የደረሰባቸው ክርስቲያኖች ጉዳታቸውን እንዳይናገሩ መከልከል ላይ ያተኮረ እንቅስቃሴ ሲፈጸም መፈጸም በሕግም በሞራልም የሚያስወቅስ ነው፡፡ ይህ በምንም ዓይነት መንገድ ፍትሐዊ ሊሆን አይችልም፡፡ ይህ ለአጥፊዎች ከለላ መስጠትን እንጂ ለፍትሕ መቆምን አያሳይም፡፡ አጥፊዎች ሲያጠፋና ክርስቲያኖችና አብያተ ክርስቲያናት ሲቃጠሉ ዝም ብሎ ማየት ትዕግሥትን ሳይሆን የጥፋት ተባባሪ መሆንን የሚያሳይ ነው፡፡

በወቅቱ የመንግሥት አካላትን ያሳስብ የነበረው የገደሉትንና አደጋ ያደረሱትን አካላት ለመያዝ ሳይሆን አደጋው በተፈጸመበት ወቅት ከቦታው ተገኝተው የዘገቡትን አካላት ለመያዝ ነበር፡፡ ይህ ተግባር አሁንም ስለቀጠለ ቤተ ክስስቲያን እየተገፋች ድምፅ የሚያሰማላት አካል እያጣች ነው፡፡ አጥፊዎች ለስንት ሺህ ዘመናት የኖረ የሀገር ሀብት ሲያወድሙ እንደ ቀልድ እየታለፈ መሆኑ ለዚህ ጥሩ ማሳያ ነው፡፡ በየካቲት ወር መጨረሻና በመጋቢት ወር መጀመሪያ በድሬደዋ ከተማ አጠገብ የሚገኘውን ደን በመመንጠር የቤተ ክርስቲያንን መሬት በመከፋፈል ላይ ሳሉ ሕግ አስከባሪ አካላት ቢደርሱም አልታዘዝንም በማለት ቆመው ሲመለከቱ አጥፊዎች ከቦታው እንዲሸሹ ሲያደርጉ እንደነበር የዐይን እማኞች ገልጠዋል፡፡ በሊሙ ኮሳ ወረዳ በያዝነው ዓመት በተፈጸመው ጥፋት ከወረዳ አመራር ጀምሮ ሥልጣን ላይ የሚገኙ ወገኖች ጥፋቱን ያደረሱት አካላት በእምነት ስለሚመስሏቸው ወደ ሕግ ለማቅረብ አለመቻላቸውን ወረዳ ቤተ ክህነቱ ለሀገረ ስብከቱ የጻፈው የድረሱልኝ ደብዳቤ ያስረዳል፡፡ ምክንያት ተፈልጐ የሚያዙትና ካለ ፍርድ እስር ቤት እንዲቆዩ የሚደረጉትም ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ ይህም ክርስቲያኖች እንዲሞቱ የተፈረደባቸው፣ ለሚደረስባቸው  አደጋ ሁሉ ከለላ የሌላቸው መሆኑን ሲያመለክት አጥፊዎች ደግሞ ሽፋን የሚሰጣቸው ይመስላል፡፡ ይህንም በሐረር ከተማ ጥር ፲፩ ቀን ፲፱፻፺፫ ዓ.ም ለጥምቀት በዓል በወጡ ምእመናን ላይ ለጁምአ ስግደት በአንድ መስጊድ ተሰብስበው የነበሩ ሙስሊሞች በፈጸሙት ትንኮሳ ግጭት ተፈጥሮ የአራት ሰዎች ሕይወት ሲያልፍ በፖሊስ ቊጥጥር ሥር የዋሉት ፲፮ ምእመናን ያለ ምንም ውሳኔ ከስድስት ወራት በላይ መቆየታቸው ማሳያ ነው፡፡ ግጭቱን ማን እንደጀመረው? ዓላማው ምን እንደነበር? አጣርቶ አስቸኳይ ውሳኔ መስጠት፣ አጥፊም በጥፋቱ እንዳይቀጥል ማስተማር ሲገባ ክርስቲያኖችን መርጦ ማሰር መፍትሔ አይሆንም፡፡ ወንጀል የፈጸመ ሰው አይያዝ ባይባልም ክርስቲያኖች ብቻ ተይዘው የሚታሰሩበት፣ ቢታሰሩም ቶሎ ለፍርድ የማይቀርቡበት ምክንያት ሌላ ዓላማ ያለ ያስመስላል፡፡

በአጥፊዎች ላይ ውሳኔ ቢሰጥበትም ቤተ ክርስቲያንን ላቃጠሉ፣ ንዋያተ ቅድሳትን ለዘረፉ አካላት የሚሰጠው ፍርድ አንድ በግ ከሰረቀ ሌባ ጋር ልዩነት የሌለው በነፃ ከማሰናበት ያልተሻለ መሆኑ ለክርስቲያኖችና ለቤተ ክርስቲያን ትኩረት መነፈጉን የሚያሳይ ነው፡፡ መረዳት የሚገባው ቤተ ክርስቲያንን አቃጥለው፣ ቅርሱን አውድመው እስከሚጨርሱ ዝም ከተባለ “ኢትዮጵያን የጎብኝዎች መዳረሻ እናደርጋለን” የሚለው አሳብ የሕልም እንጀራ መሆኑን ነው፡፡ የሚነገረው ቃልም ተፈጻሚነት ሳይኖረው ክርስቲያኖችን በማይሆን ነገር ለማዘናጋት የሚፈጸም መሆኑን የሚያሰገነዝብ ነው፡፡ ይህም በቤተ ክርስቲያን ላይ የተነሡት አፅራረ ቤተ ክርስቲያን ብቻቸውን ሳይሆኑ በጀርባቸው ሌላ አይዞህ ባይ እንዳላቸው የሚያመለክት ነው፡፡ የክርስቲያኖችና የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ትኩረት እንዳይሰጠው፣ በመገናኛ ብዙኃን ሽፋን እንዳያገኝና ሽፋን የሚያገኘውም ዘግይቶ መሆኑ ሌላ ችግር ይዞ እንዳይመጣ መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ የሚሰጠው አስተያየት እውነት የሚመስለው አጽራረ ቤተ ክርስቲያን የሚፈጽሙት እንዲሸፈን መደረጉ ነው፡፡

 በምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሜኤሶን ወረዳ በሚገኘው የአሰቦት ደብረ ወገግ ቅድስት ሥላሴና አቡነ ሳሙኤል ገዳም የካቲት ፳ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም ከረፋዱ አራት ሰዓት አካባቢ ለከብት ዘረፋ ወደ ገዳሙ ክልል የገቡ የኢሳ ጎሳ አባላትን ለመከላከል የተደረገውን የተኩስ ልውውጥ ተከትሎ ሰደድ እሳት ተቀሰቀሰ፡፡ በወቀቱ የተቀሰቀሰው ሰደድ እሳት ከ፳፻፩ ዓ.ም በኋላ ለሁለተኛ ጊዜ ነበር፡፡ ከአሥራ አምስት ዓመት በፊት ተቀስቅሶ ለ፲፭ ቀናት የቆየው ሰደድ እሳት ከ፲፩ ሺህ ሄክታር በላይ ደን አውድሟል፡፡ እሳቱ በቊጥጥር ሥር የዋለው ከዋናው የገዳሙ ግቢ ለመድረስ ፭፻ ሜትር ያህል ሲቀረው ነበር፡፡ በወቅቱ ከ፴፰ ያላነሱ ከሰል አክሳዮች ለሰደድ እሳቱ መነሣት ምክንያት ናቸው በሚል ተጠርጥረው በቊጥጥር ሥር ቢውሉም ወዲያው በዋስ ተለቀዋል፡፡ ክስ ይመሥረትባቸው አይመሥረትባቸውም የታወቀ ነገር የለም፡፡ ይህ ሁሉ የሚያሳየው በቤተ ክርስቲያንና በክርስቲያኖች ላይ ለሚደርሰው ጥፋት ማስተካከያ የሚሰጥ አለመኖሩን ያሳያል፡፡

ይቆየን!

ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ከግንቦት ፲፮-፴ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም

በዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተና

በተለያዩ መድረኮች ቤተ ክርስቲያን ከእምነት ውጭ የሆኑትን ለማሰቃየት የክፉ አድራጊዎች ጠበቃ የሆነች የሚያስመስሉ ጽሑፎች ይቀርባሉ፡፡ ድብቅ ዓላማ ያላቸው ወገኖች ቤተ ክርስቲያንንና ክርስቲያኖችን ለማጥፋት ሰበብ በመፈለግ ጥፋተኛ እያስመሰሉ ያቀርባሉ፡፡ በመሠረቱ ይህ አስተሳሰብ ሁለት መሠረታዊ ችግሮች አሉበት፡፡ የመጀመሪያው ታሪክ በመሰነድ፣ ትውልድ በምግባር ኮትኩታ ያቆየች ባለውለታ፣ ቅርሶቿ ለሀገር ልዩ መታወቂያ ጐብኝዎችን ማርኮ የሚያመጣ ሆኖ ሳለ ያለ ስሟ ስም መስጠቱ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ከእውነት የራቀ ሐሳብ ይዘው ጥፋተኛ ሳትሆን፤ ጥፋተኛ ስለሆነችና ከአጥፊዎች ስለተባበረች መጥፋት ይገባታል እንበቀላት የሚለው ነው፡፡ እነዚህ ለማጥፋት ምክንያት ፈላጊ ወገኖች ቤተ ክርስቲያንን እያቃጠሉና ምእመናንን እየገደሉ ለምን ሲባሉ ጥፋተኛ ስለሆነች ይላሉ፡፡ መቼ፣ የት፣ በማን፣ እነማንን ተብለው ሲየጠቁ መልስ የላቸውም፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ማቃጠልና ምእመናንን መግደል የእምነቱ ተከታዮች ራሳቸውን ወደ መከላከል ከዚያም ወደ መጉዳት ሊሸጋገሩ እንደሚችሉ መረዳት ይገባል፡፡ ለተፈጸመው ጥፋት አጸፋውን ቤተ ክርስቲያን ብትመልስ በሀገር ላይ ሊከሠት የሚችለውን ጥፋት አስቀድሞ መረዳትም ይጠቅማል፡፡ ጥናትን ሽፋን አድርጎ ለአጥፊዎች ዱላ የሚያቀብሉ አካላትም ከድርጊታቸው መቆጠብ ይኖርባቸዋል፡፡ መንግሥት አጥፊዎችን ለሕግ ከማቅረብ በተጨማሪ ለክርስቲያኖችና ለቤተ ክርስቲያን ከለላ መስጠት ይኖርበታል፡፡ አጥፊዎችም ክርስቲያኖችን ለማጥፋት የመዘዙት ሰይፍ ወደ ራሳቸው እንዳይዞር እና የእርስ በእርስ መጠፋፋት ሊያስከትል እንደሚችል ደጋግመው ሊያስቡበት ይገባል፡፡ በሃይማኖትና በዘር ምክንያት የተቀሰቀሰ ግጭት መብረጃ እንደሌለው በየሀገራቱ የተፈጸሙትን ጥፋቶች ማየት ይገባል፡፡ ታሪክ መጥቀስ ብቻውን የዕውቀት ባለቤት አያደርግም ከታሪክ መማር እንጂ፡፡

ከ፲፱፻፷፮ ዓ.ም ወዲህ በቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሰውንና ከዛሬ ነገ እርምት ይወስድበታል በማለት በትዕግሥት ስትጠብቅ መኖሯን ከመግለጻችን በፊት ቤተ ክርስቲያን ለሀገር ያበረከተችውን አስተዋጽኦ በመጠኑ ለመዳሰስ እንሞክራለን፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሰዎችን ለመንግሥተ ሰማያት ስታዘጋጅ፣ በፍቅር ስባ፣ በትምህርት አለዝባ በእምነትም በምግባርም እንዲስተካከሉ በማድረግ ነው፡፡ ከአፍሪካ ሀገራት መካከል ሀገራችን ብቸኛ የራሷ ፊደል ያላት፣ ዘመን ተሻግሮ ከዘመናችን የደረሰ ቅርስ አበርክታ ሀገራችን በመላው ዓለም እንድትታወቅ ያደረች ባለውለታ ናት፡፡ አፍሪካውያን በቅኝ ግዛት ሲማቅቁ ኢትዮጵያውያን የቅኝ ግዛት ቀንበርን ሰብረው ጥለው፣ የነጭን ትምክተኛነት አስተንፍሰው ልጆቻቸው ቀና ብለን እንድንሔድ የመሪነቱን ሚና የተጫወተች ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ በውጭ ሀገራት በልዩ ልዩ ቋንቋዎች ተጽፈው እምነት፣ ዕውቀት፣ ሥነ ምግባር የሚያስተምሩ መጻሕፍት ኢትዮጵያዊ በሆነ ብሂል ተተርጒመው ትውልድ እንዲማርባቸው፣ ሊቃውንቶቿ በአፍሪካ፣ በመካከለኛው ምሥራቅና በአውሮፓ የኢትዮጵያን ባህል፣ ሃይማኖት፣ ታሪክ በማስተዋወቅ የአምባሳደርነት ሚና እንዲጫወቱ ያደረገችው ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ይህን የቤተ ክርስቲያን አስተዋጽኦ ዶክተር አክሊሉ ሀብቴ ‹‹የኢትዮጵያ ምሁራን መነኮሳት በኢትዮጵያ መልክዓ ምድር ክልል ውስጥ ብቻ ሳይሆን ከዚያም ውጭ በመሔድ በታሪክ ሊታወስና ሊጠና የሚገባ አስተዋጽኦ አበርክተዋል፡፡ በኢትዮጵያ አካባቢ በሱዳንና በግብፅ፣ በየመንና በኢየሩሳሌም፣ በአውሮፓ በመሔድ እነሱም እየተማሩ፣ የውጭውንም ሕዝብ ስለ ኢትዮጵያ ቋንቋና ታሪክ፣ ሃይማኖትና ባህል እንዲያውቅና እንዲፅፍ አድርገዋል›› (አክሊሉ፤፹፩) በማለት ገልጠውታል፡፡

እውነተኞቹ ተመራማሪዎች ያለ ኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ኢትዮጵያን ማሰብ እንደሚከብድ በምርምራቸው አረጋግጠው እውነቱን ከሐሰት፣ ብስሉን ከጥሬ፣ የሚጠቅመውን ከሚጐዳው፣ የተፈጸመውን ካልተፈጸመው ለይተው ከጥንካሬያችን እንድንማር ከስሕተታችን እንድንጠበቅ ያደረጋሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ማዳከም ዓላማችንን ያሳካልናል ብለው የሚያስቡ ወገኖች ደግሞ ኢትዮጵያን ቅኝ ለመግዛት ፈልገው ቅስማቸው ተሰብሮ እንዲመለስ ያደረገችው ቤተ ክርስቲያን መሆኗን ስለተረዱ ስሟን ለማጥፋት፣ ታሪኳን ለመበከል የጻፉትን አሉባልታ እውነት አድርገው በመውሰድ ታሪክ ሲያበላሹ፣ በተቀመጡበት የኃላፊነት ቦታ ጥፋት ሲፈጽሙ ይታያሉ፡፡ ሰውን በሰውነቱ እኩል ማገልገል ሲገባቸው በጎሳ፣ በቋንቋ፣ በጎጥ፣ በቡድንና በባህል በመከፋፈል ሥልጣንን ለክፉ ተግባር ይጠቀማሉ፡፡ ሕዝብን ለማገልገል የተሰጣቸውን ሥልጣን ተጠቅመው ቤተ ክርስቲያንንና ምእመናንን የማሳደድ ተልእኮ ይፈጽማሉ፡፡ ሀገር ሰላም ካልሆነችና ዜጎቿ በሰላም ወጥተው ካለገቡ አጥፊዎችም ችግር እንደሚገጥማቸው አልተረዱትም፡፡

በካናዳ፣ በቫቲካን፣ በጀርመንና በሌሎችም ሀገሮች የኢትዮጵያ ጥናት ተቋማት እንዲከፈቱ፣ ተመርምሮ የማያልቅ ዕውቀት የያዙት የብራና መጻሕፍት ለዓለም እንዲተዋወቁ ያደረጉት ቤተ ክርስቲያናችን አስተምራ «ሑሩ ወመሀሩ» ብላ ያሰማራቻቸው ሊቃውንት ናቸው፡፡ በሌላ በኩልም ሀገራችን እንግዳ ተቀባይ የሆነችውና ዓለም ፊቱን ያዞረባቸውን የመሐመድ ተከታዮች ሳይቀር መጠጊያ እንድትሆን ያደረጋት ቤተ ክርስቲያን በእምነት ኮትኩታ፣ በምግባር አንፃ ያስተማረቻቸው እነ ንጉሥ አርማህ ርኅሩኆች ብቻ ሳይሆኑ አስጠጉኝ ብሎ የመጣባቸውን አሳልፈው ለመስጠት ሰብአዊነት የተለያቸው ስላልነበሩ ጭምር ነው፡፡

ወርቅ ላበደረ ጠጠር፣ እህል ላበደረ አፈር እንዲሉ ይህን ውሉ ውለታ ለዋለች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተሰጠው መልስ ነው፡፡ የደረሱበት መረጃ ካለ ማስረጃን መሠረት አድርጎ እውነት ማሳወቅ አንድ ነገር ነው፣ ሐሰትን እውነት እያስመሰሉ ማቅረብና ሰውን ለብጥብጥ መጋበዝ ግን ጤነኛ አእምሮ ያለው፣ በእግዚአብሔር የሚያምን ሰው የሚፈጽመው አይደለም፡፡ በየጊዜው ቤተ ክርስቲያንን የሚያቃጥሉት፣ ክርስቲያኖችን የሚገድሉት፣ ንብረታቸውን የሚቀሙትና የሚያሳድዱት ከመጥፎ ድርጊታቸው እንዲታቀቡ መንግሥት እርምት ይወስዳል ቢባልም ምንም ነገር እንዳልተፈጸመ እየታለፈ፣ የማዘናጊያና የማረሳሻ ተግባር እየተፈጸመ ነው፡፡

ከምዕራባውያን የተኮረጀው ሥርዐተ ትምህርት ባልነበረበት ዘመን የሀገራቸው አምባሳደር የነበሩ፣ የውጭ ዲፕሎማት ሲመጣ አስተርጓሚ ሆነው ሲያገለግሉ የኖሩ ሊቃውንትን ያፈራችን ቤተ ክርስቲያን ከዋለችበት ላለማሳደር፣ ካደረችበት ላለማዋል እየተፈጸመ ያለው ግፍ መቆም አለበት፡፡ የሊቃውንቱን አስተዋጽኦ አክሊሉ ሀብቴ ‹‹ሆኖም እዚያ (ኢየሩሳሌም) የተደራጀው የመነኮሳት ማኅበር ኢትዮጵያን በመወከል ወደ ኢጣሊያም፣ ወደ አርመንም፣ ወደ ቊስጥንጥንያም፣ በመሔድ ግንኙነት ፈጥሮ እንደነበርና ምን አልባትም ከአርመኖች ጋር በነበረው የቅርብ ግንኙነት አርመኖች ፊደላቸውን ሊቀረፁ የቻሉት ከኢትዮጵያ ፊደል እንደሆነም ይነገራል፡፡ ወደ ኢየሩሳሌም በሚመላለሱበት ዘመን እግረ መንገዳቸውንም ከሱዳንና ከግብፅ ክርስቲያኖች ጋር የቅርብ ግንኙነት መፍጠራቸው ይታመናል፡፡ የቀድሞዎቹ የኢትዮጵያ ምሁራን መነኮሳት ፈር ቀዳጅ አስተዋጽኦ እንዲሁ መጠናት የሚገባው ነው›› (አክሊሉ፣ ፷፪) በማለት ገልጠውታል፡፡

ቤተ ክርስቲያን ልጆቿ ሰው አክባሪ፣ ሀገር ወዳድ፣ የሥራ ፍቅር ያላቸው፣ የራሳቸውን የማያስነኩ፣ የሌላውን የማይፈልጉ አድርጋ ስታሳድጋቸው ጠብ አጫሪነትን፣ በጉልበታቸው የሚመኩ መሆንን እንዲጸየፉ በማድረግ ነው፡፡ ጠላታቸውን በጽናትና በትዕግሥት እንዲቋቋሙ፣ ሀገርና ሃይማኖት ሊያጠፋ የመጣውን የጥፋት ኃይል እንዳያሸንፍ ያደረገች ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ይህ ድርጊቷ ያበሳጫቸው ምዕራባውያን በዘመናዊ ትምህርት ሰበብ በየሴሚናሪዎቻቸውና ኮሌጆቻቸው አስተምረው የላኳቸው ወገኖቻችን ነባሩን የኢትዮጵያ ሃይማኖትና፣ የክርስቲያኖች ተጋድሎ የሚያናንቅ፣ መልኩ የእኛ ቢሆንም የነጭ ጉዳይ አስፈጻሚ ሀገሪቱን ለባዕድ አሳልፎ ለመስጠት የባለቤትነት ስሜት የሚያድርበት እንዳይሆን አእምሮውን ለውጠው ሲልኩት ኖረዋል፡፡ በመመረቂያ ጽሑፍ ሰበብ ቤተ ክርስቲያንን ያለ ስሟ ስም፣ ያለ ግብሯ ግብር እየሰጡ የዘመናችን ተመራማሪ ነን ባዮች የግብር አባት ሆኑ፡፡ በዚህ ተግባራቸውም ትውልዱ በሰላም ውሎ እንዳይገባ እንቅልፍ ላጡ ወገኖች መንገድ መሪ የጥፋት ተባባሪ ሆነው አልፈዋል፡፡ ይህን ለማረጋገጥ ራሳቸውን ተሐድሶ ብለው የሠየሙ አካላት በተለያዩ የኅትመትና የብሮድካስት ሚዲያዎች በቤተ ክርስቲያን ላይ የሚያወርዱትን የስድብ ዶፍ መመልከት ይቻላል፡፡ በአካል መግዛት ያልተቻላቸውን ኢትዮጵያውያንን በአእምሮ ለመግዛት መሰሎቻችንንና በሥጋ የሚዛመዱንን አእምሮ እየለወጡ የሚልኩልንንና እነሱም አልፎ ሒያጅ መንገደኞችና ለቤተ ክርስቲያን ጥላቻ ያደረባቸውን ወገኖች እየጠየቁ የጻፉትን አሉባልታ በትክክለኛ ማስረጃ በመሞገት፣ የዕውቀታቸውን ግልብነት፣ የመረጃቸውን ተራነት፣ የትነታኔያቸውን አመክንዮ አልባነት ማሳየት ይኖርብናል፡፡ አጥፊዎች ታጥቀው ሲዘምቱብን ዝም ብሎ ማየት እሳት መቃጠሉን የሰማ የዋህ እኔስ ሣር ውስጥ ተደብቄያለሁ በማለት የመለሰውን የሚያስታውስ ይሆናል፡፡

ቱሪስቶች ሊጐበኙ የሚመጡት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ገዳማት፣ አድባራት፣ ሥዕላት፣ የብራና መጻሕፍትና ንዋያተ ቅድሳት እንዲሁም ክርስቲያን ነገሥታት የገነቧቸውን አብያተ ክርስቲያናት፣ ሐውልቶችና አብያተ መንግሥታት ለመጎብኘት ነው፡፡ ይህን አስተዋጽኦ ያደረገችልን ቤተ ክርስቲያን መደገፍና መጠበቅ ሲገባ ስትጠቃ ዝም ብሎ ማየት ማሯን እንጂ ንቧን አልፈልግም እንደ ማለት ይቈጠራል፡፡ ለጥፋት የተሰለፉ ወገኖች በቤተ ክርስቲያንና በምእመናን ላይ አደጋ ሲያደርሱ የግለሰቦች ጉዳይ እየመሰለ ይቀርባል፡፡ በመገናኛ ብዙኃን ይነገራል፡፡ በሌሎች እምነቶች ላይ የሚፈጸመው ወይም ራሳቸው ፈጽመው ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮሃል የተባለውን ለሚፈጽሙት ግን ከመገናኛ ብዙኃን ጀምሮ የሚሰጠው ሽፋን የሚገርም ነው፡፡ ይህም ክርስቲያኖች ሲገደሉ፣ አብያተ ክርስቲያናት ሲቃጠሉ መረጃው በቶሎ እንዳይነገር ከተቻለም ተዳፍኖ እንዲቀር ለማድረግ እየተሠራ መሆኑን እንድንጠረጥር የሚያደርግ ነው፡፡ ለምሳሌ በቡኖ በደሌ የተፈጸመውን ሰቆቃ በሥልጣን ላይ የተቀመጡ አካላት ወንጀሉን የፈጸሙት አካላት በእምነት ስለሚመስሏቸው ለማዳፈን ሞክረዋል፡፡ በሰሜን ሸዋና በኬሚሴ በክርስቲያኖችና በአብያተ ክርስቲያን ላይ የደረሰው ጥፋት በመገናኛ ብዙኃን የተነገረው ጥፋቱ ከተፈጸመ ከአራት ቀናት በኋላ መሆኑን ኢትዮጲስ ጋዜጣ በሚያዝያ ፮ ዕትሙ አስነብቧል፡፡ በበሻሻ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ እና አካባቢው አብያተ ክርስቲያን ተቃጥለውና ምእመናን ተገድለው አጥፊዎችን መያዝ ሲገባ መረጃው ያላቸውን ክርስቲያኖች ለመያዝ ይደረግ የነበረው ወከባ የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡

ይቆየን!

ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ከግንቦት ፲፮-፴ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም

ሰሙነ ሕማማት (ከዕለተ ሰኑይ እስከ ቀዳሚት ሰንበት)

በመምህር ቸርነት አበበ

መጋቢት ፳፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

መግቢያ

ከአባታችን አዳም በደል ወይም ስሕተት በኋላ በሕማማት፣ በደዌያት፣ በመቅሠፍታት፣ ወዘተ በብዙ መከራ የሰው ልጅ ሊኖርባቸው ግድ የኾነባቸው ዘመናት ጥቂቶች አልነበሩም፡፡ የሰው ልጅ ቢያጠፋ፣ ቢበድል፣ ከሕገ እግዚአብሔር ቢወጣ እንኳን የዋህ፣ ታጋሽ፣ ቸር፣ አዛኝ የኾነው አምላክ የጠፋውን ሊፈልግ፣ የተራበውን ሊያጠግብ የታረዘውን ሊያለብስ፣ ፍቅር ላጣው ፍጹም ፍቅር ሊለግስ፣ ሰላም ለሌለው ፍጹም ሰላም ሊሰጥ፣ ተስፋ ለሌለው ተስፋ ሊያጐናጽፍ ከሰማይ ወረደ፤ ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደ፤ በገዳመ ቆሮንቶስ ዐርባ ቀንና ሌሊት ጾመ፡፡ በጾሙም የኀጢአት ሥሮች ወይም ራሶች የተባሉትን ስስትን፣ ትዕቢትንና ፍቅረ ንዋይን ድል አደረገልን፡፡ እኛ እርሱ የጾመውን ጾም እንድናከብር እንድንጾም ምሳሌ ኾነን፡፡ ዲያብሎስን ድል አድርጐ ድል እንድንነሣው ኃይልና ምሳሌ ኾነን፡፡

ሰሙነ ሕማማት ምንድን ነው?

‹ሰሙን› – ‹‹ሰመነ ስምንት (ሳምንት) አደረገ›› ማለት ነው፡፡ ይኸውም ከዕለተ ሆሣዕና ሠርክ እስከ ትንሣኤ ሌሊት ያለውን ጊዜ ወይም ቀናት የሚያመለክት ነው፡፡ ‹ሕማም (ሕማማት)› – ‹ሐመ ታመመ› ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲኾን ይህም የሰውን ዘር ዂሉ ከዲያብሎስ ባርነት ነጻ ለማውጣት ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፈቃዱ የተቀበላቸውን ጸዋትወ መከራዎች የሚያሳስብ ነው፡፡ ዕለታቱ የዓመተ ኵነኔ ወይም የዓመተ ፍዳ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ክርስቲያኖች የክርስቶስን ውለታ እያሰቡ እጅግ የሚያዝኑበት፣ የሚያለቅሱበት፣ የሚሰግዱበት ቤት ንብረታቸውን ትተው ከሌላው ቀናትና ጊዜያት በተለየ መልኩ ቤተ ክርስቲያናቸውን የሚማጸኑበት፤ ጧት ማታ ደጅ የሚጠኑበት፤ ኀጢአታቸውን በቤተ ክርስቲያን አደባባይ ለካህኑ የሚናዘዙበት በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ የሚገኝ ሳምንት ነው፡፡

በዚህ ሳምንት ብዙ አዝማደ መባልዕት አይበሉም፤ ይልቁን በመራብ በመጠማት በመውጣት በመውረድ በመስገድ በመጸለይ በመጾም በየሰዓቱ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ጸዋትወ መከራዎች በማሰብ አብዝቶ ይሰገዳል፡፡ መከራውን፣ ሕማሙን፣ ድካሙን የሚያስታውሱ ከቅዱሳት መጻሕፍት ኢሳይያስ፣ ኤርምያስ መዝሙረ ዳዊት፣ ግብረ ሕማማት ወዘተ በየሰዓቱ ይነበባል፡፡ መስቀል መሳለም የለም፡፡ ካህናትም ‹‹እግዚአብሔር ይፍታህ›› አይሉም፡፡ ሥርዓተ ፍትሐት አይፈጸምም፡፡ ይኸውም ይህ ሳምንት ከሞት ወደ ሕይወት የተሸጋገርንበት ከጨለማ ወደ ብርሃን የተጓዝንበት የመሸጋገሪያ ወቅት ምሳሌ በመኾኑ ነው፡፡ በዕለተ ምጽአት መላእክት የመለከት ድምፅ በማሰማት የዳግም ምጽአትን ዕለት ለማሳሰብ ምእመናን ጥሪውን ሰምተው ለዚህም አስቀድመው ተዘጋጅተው የበዓሉ ታዳሚዎች መኾናቸውን በማጠየቅ በዚህ ሳምንት ዲያቆኑ ቃጭል እየመታ በየሰዓቱ ምእመናኑን ያሳስባል፡፡ Read more