‹‹ጥልንም በመስቀሉ ገደለ›› ኤፌ.፪፥፲፮

የዓለም ሰላም የተሰበከውና የተረጋገጠው በመስቀል ላይ በተደረገው የክርስቶስ ቤዛነት ነው፡፡ ለዚህም ነው ሐዋርያው ‹‹ጥልን በመስቀሉ ገድሎ ርቃችሁ ለነበራችሁ ሰላምና የምሥራችን ሰበከ›› ያለው….

መስቀል

መስቀል ነገር በመጀመሪያ የተገለጸው በመላእክት ዓለም ነበር፡፡

መስቀል የሰላም መሠረት ነው

መስቀል  የሰላም መሠረት፤ ሰላምም የመስቀል ፍሬ ነው፡፡ በግእዝ ሰላም የሚለው ቃል ትርጉም ‹‹ፍጹም ጤና፣ ዕረፍት፣ እርቅ፣ ሰላምታ፣ የቡራኬና የምርቃት ቃል፣ ሰው ሲገናኝና ሲለያይ የሚናገረው›› ነው፡፡ መስቀልና ሰላም አንዱ የአንዱ መሠረት አንዱ የአንዱ ፍሬ ሆነው የተሳሰሩትም በዚህ ምክንያት ነው፡፡

ኦርቶዶክሳዊ መንፈሳዊነት

ክርስትና የሕይወት መንገድ ነው፡፡ መንገዱም ደግሞ ወደ ዘላዓለማዊ ክብር የሚያደርስ የሕይወት የድኅነትና የቅድስና መንገድ ነው፡፡ ክርስቲያን ለመሆን በ፵ እና በ፹ ቀን በመጠመቅ የሥላሴ ልጅነትን ማግኘት የቤተ ክርስቲያን አባል መሆን ያስፈልጋል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ዳግመኛ መወለድ ማለትም ነው፡፡

ዘመነ ፍሬ

ከመስከረም ፱ እስከ ፲፭ ያሉት ዕለታት ዘመነ ፍሬ ተብለው ይጠራሉ፡፡ በእነዚህ ወቅት የሚዘመረው መዝሙርም ሆነ የሚነበቡት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች እግዚአብሔር ለምድር ፍሬንና ዘርን የሚሰጥ የዓለም መጋቢ መሆኑን የሚያስገነዝቡ ናቸው፡፡

ዘመነ ቅዱስ ዮሐንስ

ርእሰ ዐውደ ዓመት

ዲያቆን ዘክርስቶስ ፀጋዬ

የኢትዮጵያ ዘመን መለወጫ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት መሠረት መስከረም አንድ ቀን ይከበራል፡፡ ስያሜው ቅዱስ ዮሐንስ በመባል ሲታወቅ ከመስከረም አንድ እስከ ስምንት ድረስ ያሉት ዕለታትንም ያካትታል፡፡ በዚህ ወቅት በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው መዝሙር ክብረ ቅዱስ ዮሐንስንና ርእሰ ዐውደ ዓመትን የሚያወሳ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ያስተማረውን ትምህርትና ገድሉን የሚያመለክት ስብከት ይሰበካል፤ ትምህርቱም ይሰጣል፡፡ አዲስ ዓመት ዘመን መለወጫ በመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ስም የተሰየመበት ምክንያት፡-

፩. የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ተግባር ለዘመነ ወንጌል መነሻ በመሆኑ

ቅዱስ ማርቆስ በወንጌሉ ‹‹እነሆ÷ መንገድህን በፊትህ የሚጠርግ መልክተኛዬን በፊትህ እልካለሁ፡፡ የእግዚአብሔርን መንገድ ጥረጉ፤ ጥርጊያውንም አስተካክሉ እያለ በምድረ በዳ የሚጮኽ የአዋጅ ነጋሪ ድምጽ፤ ዮሐንስም በምድረ በዳ ያጠምቅ ነበር፤ ኃጢአትንም ለማስተስረይ የንስሓ ጥምቀትን ይሰብክ ነበር፡፡ የይሁዳና የኢየሩሳሌምም ሰዎች ሁሉ ወደ እርሱ ይሄዱ ነበር፤ ኃጢአታቸውንም እየተናዘዙ በዮርዳኖስ ወንዝ ሁሉንም ያጠምቃቸው ነበር»  (ማር.፩፥፪-፭) ብሎ ጽፎልናል፡፡ የካህኑ ዘካርያስ ልጅ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ በዘመነ ብሉይ መጨረሻና በዘመነ ሐዲስ መጀመሪያ ላይ ተነስቶ «መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሓ ግቡ›› እያለ ስለ ክርስቶስ አዳኝነት በምድረ በዳ እያስተማረና የንስሓ ጥምቀት እያጠመቀ በዘመነ ወንጌል መጀመሪያ ምዕራፍ ተገኝቷል፡፡ እንዲሁም መጥምቁ ዮሐንስ በነቢያት መጨረሻ በሐዋርያት መጀመሪያ ተገኝቶ ዘመነ ሐዲስን እንደሰበከና ከዘመነ ብሉይ ወደ ዘመነ ሐዲስ መሸጋገሪያ ጊዜ ላይ ስለነበረ ያለፈውን ዘመን የምንሸጋገርበት የዘመን መለወጫ ቀን የቅዱስ ዮሐንስ መታሰቢያ እንዲሆን ተደርጓል፡፡

፪. መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ የጻድቃን የሰማዕታት ርእስ ነውና

በቅዱስ ማቴዎስ ወንጌል ላይ ‹‹እውነት እላችኋለሁ፤ ሴቶች ከወለዱአቸው ወገን ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሣም›› (ማቴ.፲፩፥፲፩) ብሎ ጌታችን ስለ ዮሐንስ በተነገረለት መሠረት የጻድቃን የሰማዕታት ርእስ እንደመሆኑ አዲስ ዓመትም የበዓላት ሁሉ በኩር ርእስ ነውና በስሙ ተጠርቷል፡፡ እንደዚሁም ጌታ ባረገ በ፻፹ ዘመን በእስክንድርያ ፲፪ ሊቀ ጳጳሳት ሁኖ የተሾመው ቅዱስ ድሜጥሮስ  ባሕረ ሐሳብን ሲደርስ ከዮሐንስ ጀምሮ ደርሶታል፤ ሲጨርስም ለኢየሩሳሌም፣ ለሮም፣ ለኤፌሶንና ለአንጾኪያ ሊቃነ ጳጳሳት ልኳል፡፡ በእስክንድርያ /ግብጽ/ በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር በዓላት የሚከበሩትና አጽዋማት የሚገቡት ከመስከረም አንድ ተነስቶ በመቁጠር ነው፡፡  በቤተ ክርስቲያናችን የበዓላቱና የአጽዋማቱ መደብ የሚታወቅበትና የዘመናቱ ሂደት ተቀምሮ የሚታወጅበት መስከረም አንድ በመሆኑ ርእሰ ዐውደ ዓመት ይባላል፡፡ ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድም የዘመን መለወጫን አዲስ ዓመት በዓል አስመልክቶ እንደነገረን ‹‹ርእሰ ዐውደ ዓመት ዮሐንስ ወላዴ መጥቅዕ ወአበቅቴ፤›› የዓመት በዓል ራስ ዮሐንስ መጥቅዕና አበቅቴን የምትወልድ ነህ›› እየተባለ ይዘመርለታል፡፡

ጾመ ዮዲት

ዲያቆን ዮሴፍ በቀለ

በናቡከደነጾር ዘመነ መንግሥት ንጉሡ ሥልጣኑን መከታ በማድረግ የእግዚአብሔርን ሕዝብ በግድ እያስገደደ እጅ መንሻ ይቀበል ነበር፡፡ የመንግሥቱን ትእዛዝ ያልተቀበለውንም እየገደለ፣  ጭፍሮቹ ኃያልነቱንና ገናናነቱን በዓዋጅ በጦር አዛዦች ጭምር እያሳወጀ፣ በርካታ የጦር ሠራዊቶችን አሰልፎ ከአይሁድ ከተማ ገባ፡፡ በዚያም ነዋሪዎችን በማስፈራራት የመንግሥቱን ትእዛዝ ያልተቀበሉትን ሁሉ እያሳደደ ስላስጨነቃቸው ማቅ ለብሰው፣ አመድ ነስንሰውና ድንጋይ ተንተርሰው ወደ ፈጣሪያቸው በመጮህ መለመን ጀመሩ። በጭካኔ የተሞላው የጦር አበጋዙ ሆሎፎርኒስም ይበልጥ እጅግ እንዲሰቃዩ ውኃ የሚቀዱበትን ስፍራ ተቆጣጠረው፤ በግዴታ ማርኮም እጅ እንዲሰጡ እንዳደረጋቸው በመጽሐፈ ዮዲት ፪፥፪ ላይ ተጽፏል፡፡ በአካባቢው ይኖር የነበረ ዖዝያን የተባለ አንድ ሰው የአባቶቻቸው አምላክ ጸሎታቸውን እንዲሰማቸው ለአምስት ቀናት በትዕግሥት ይጾሙና ይጸልዩ ዘንድ ሕዝቡን መከራቸው፤ እነርሱም በትዕግሥት ሊጠብቁ ተስማሙ፡፡

የእስራኤል ልጆች የናቡከደነጾርን ጦር ብንችል ተዋግተን እንረታለን፤ ካልሆነም እጅ እንሰጣለን በማለት ይመካከሩ ጀመር። በዚያን ጊዜ ባሏ የሞተባትና በንጽሕና ተጠብቃ፣ በጸሎትና በሕገ እግዚአብሔር የምትኖር ዮዲት የተባለች ሴት ነበረች። (ዮዲት ፯፥፲) እግዚአብሔርን የምትፈራ ብቸኛዋ ሴት እርሷ ነበረችና ምክክራቸውን ስትሰማ ለምን «እግዚአብሔር ያድነናል አትሉም» ብላ ገሠጸቻቸው፡፡ ማቅ በመልበስ፣ አመድ በመነስነስና ድንጋይ በመንተራስም ሱባኤ ገባች። በሦስተኛው ቀንም እግዚአብሔር አምላክ ሕዝቧን የምታድንበትን ጥበብ ገለጸላት፤ ዮዲትም እግዚአብሔር የሰጣትን ውበት ተጠቅማ ሕዝቧን ከጥፋት የምትታደግበትን ጥበብ ተረዳች።

የክት ልብሷን ለብሳ፣ ሽቱ ተቀብታና ተውባ የጠላት ሠራዊት ወዳሉበት የጦር ሰፈር በድፍረት አመራች፡፡ ሠራዊቱም ውበቷን አይተው እጅግ በመደነቅ «ይህችስ ለአለቃችን ትገባለች» ተባብለው ከጦር መሪያቸው ዘንድ ወሰዷት። እርሷም ቀድማ ማምለጫ መንገድ አዘጋጅታ ነበርና ወደ አዛዡ ከገባች በኋላ «ክቡር ጌታዬ ሆይ ርስት ተወስዶብኛል፤ እንድትመልስልኝ አስቀድሜ ደጅ ልጠና መጥቻለውና ርዳኝ፤ ትብብርህ አይለየኝ» አለችው፡፡ በስሜት ፈረስ ታውሮ የነበረው የሠራዊቶቹ አዛዥም የጠየቀችውን እንደሚፈጽምላት ቃል ገባላት። ባማረ ድንካን እንዲያስቀምጧት ሎሌዎቹን አዘዘ። ዮዲትም የተሰጣትን ጥበብ ተጠቅማ፣ መውጣት ስትፈልግ የምትወጣበትን እና የምትገባበትን ዕድል በእግዚአብሔር አጋዥነት ዐወቀች፡፡ ከቀናት በኃላ የጦር አበጋዙ ለሠራዊቱ የምሳ ግብዣ አዘጋጅቶ ዮዲትን ከጎኑ አስቀመጣት፤ ከበሉና ከጠጡ በኋላም ሁሉን ሰው አስወጣ፤ እልፍኙን በመዝጋት ከእርሷ ጋር ብቻውን ሆነ፤ ነገር ግን እንቅልፍ ጣለው፡፡ (ዮዲት ፰፥፪) እርሷም ወደ አምላኳ ጸለየች፤ ፈጣሪዋ እንዲረዳትም አጥብቃ ለመነች። በኋላም ከራስጌው ሰይፍ አንስታ አንገቱን ቀላችው፤ በድኑንም ከመሬት ጣለችው። የሆሎፎርኒስን ሞት ሠራዊቱ ሲሰሙ አውራ እንደሌለው ንብ ተበተኑ፤ ከፊሎቹ ሞቱ። እስራኤላውያንም ከሞት ተርፈው በእግዚአብሔር ኃይል ድል አደረጉ፤ በደስታም ፈጣሪያቸውን አመሰገኑ።

ይህ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ታሪክ የሚያስረዳን ዮዲት ጠላቶቿን ድል ያደረገችው በጾምና በጸሎት እንደሆነ ነው፡፡ ለእኛም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች ምንም እንኳ ወርኃ ጳጉሜን የፈቃድ ጾም ቢሆንም በሀገራችን የተጋረጠውን ችግር እናልፍ ዘንድ በፈቃደኝነት እንጾማለን። እግዚአብሔር አምላካችን ለሁላችንም ጥበብ ሰጥቶናል። ይህም ችግሮችን ሁሉ የምንፈታበት መንገድ ነው። በዚህም የዓመተ መሸጋገሪያና የክረምቱ ወር ማብቂያ በመሆኑ ዕለተ ምጽአት ስለሚታሰብበት በየዓመቱ በጳጉሜ ወር ከሌሊት ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን ተገኝተን ጠበል በመጠመቅ፣ በማስቀደስና በመጸለይ እንዲሁም ሥጋ ወደሙን በመቀበል ልናሳልፍ ይገባል። ዕለተ ምጽአትም ከዚህ ዓለም ወደ ወዲያኛው ዓለም መሸጋገሪያችን ነውና በቀኙ እንቆም ዘንድ እንጾማለን፡፡ የሚመጣውን አዲስ ዘመንም በንጽሕና ለመቀበል ስላለፈው ዓመት ኃጢአታችን ንስሓ የምንገባበት ጾምም ነው።   

ከተጋረጠብን ችግር «እግዚአብሔር ያድነናል» በማለት ልክ እንደ ዮዲት ሱባኤ ገብተን፣ ማቅ ለብሰን፣ አመድ ነስንሰንና ድንጋይ ተንተርሰን አብዝተን ልንጾምና ልንጸልይ ይገባል፡፡ ሊለያየን፣ ሊነጣጥለን፣ ሊበታትነን እና ሊገድለን ካሰበው እንዲሁም ፍቅርን፣ መተሳሰብንና አንድነትን ሊነፍገን ከቃጣው ጠላትና ሃይማኖታችንን ሊያስተወን ከሚመጣ ፀረ ሃይማኖት እንድናለን። ስለዚህ ከፊታችን ያለችውን ስድስቱን የጳጉሜን ቀን በፍቅር፣ በአንድነትና በሃይማኖት ጸንተን፣ ጾመን፣ ጸልየን ለዘመነ ዮሐንስ እንድንደርስ እግዚአብሔር አምላካችን ይርዳን፤ አሜን።

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ጎሐ፤ ጽባሕ

ዲያቆን ዘክርስቶስ ፀጋዬ

ጎሐ ፤ ጽባሕ ከነሐሴ ፳፱ እስከ ጳጉሜ ፭ ድረስ ያሉት ቀናት የሚጠሩበት ነው፤ ጎሐ ማለት ነግህ ሲሆን ጽባሕ ደግሞ ብርሃን ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድ በድጓው «ዘመናትን የምታፈራርቅ፤ የብርሃንን ወገግታ የምታመጣ አንተ ነህ» እያለ በመግለጽ ዓለምን ካለመኖር ወደ መኖር ያመጣው፣ ከመኖርም ወደ አለመኖር የሚያሳልፍ፣ በጨለማ መካከል ብርሃንን ያደረገ እርሱ መሆኑን ያስረዳል፡፡ ብርሃን እና ቀን የልደት፣ ሌሊትና ጨለማን የሞት ምሳሌዎች ሆነው ያገለግላሉ፡፡

ከነሐሴ ፳፱  እስከ ጳጉሜ ፭ ድረስ ያለው ወቅት የክረምቱ ጨለማ የሚወገድበት፣ የፀሐይ ብርሃን ወለል ብሎ የሚወጣበት፣ ጉምና ደመና በየቦታቸው ተሰብስበው፣ ሰማይ በከዋክብት አሸብርቆ የሚታይበት ነው፡፡

በክረምቱ ውኃ ሙላት ምክንያት ግንኙነት አቋርጠው የነበሩ ወገኖች ሁሉ በዚህ ክፍለ ጊዜ ብርሃን ስለሚያዩ፤ መገናኛ መንገዶችም ስለሚያገኙ፣ ክረምቱን እንደ ሌሊት በመመልከት ይህን ወቅት እንደ ንጋት መታየቱን ለመግለጽ ቤተ ክርስቲያን ‹‹ጎሐ፤ ጽባሕ›› በሚለው ስያሜ ትጠራዋለች፡፡ በዚህ ወቅት የሚዘመሩ መዝሙራት ‹‹አቤቱ ወደ አንተ እጸልያለውና በማለዳ ድምፄን ስማ›› (መዝ.፭፥፪)፤ በጨለማ የተቀመጠው ሕዝብ ብርሃንን አየ፣ በሞት ጥላ ሥር ለተቀመጡት ብርሃን ወጣላቸው (ማቴ.፬፥፲፮) የሚሉትና የመሳሰሉት ናቸው፡፡

በአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን (ጸሎተ ሃይማኖት)

ቤተ ክርስቲያን ሰማያዊት ንጽሕትና ቅድስት የክርስቶስ ማደሪያ ናት፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ «በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቋት ዘንድ እናንተን ጰጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለራሳችሁ እና ለመንጋው ሁሉ ተጠንቀቁ» በማለት ያስጠነቅቃል፡፡ በሰው ልጅ ፈቃድና ሐሳብ ያልተሠራች እግዚአብሔር በደሙ የዋጃት ቅድስት ሥፍራ ናት፡፡ ቤተ ክርስቲያን በሰማይና በምድር ያለች፣ ከሰው ልጅ ዕውቀት ፈቃድና ፍላጎት በላይ የሆነች የእግዚአብሔር ማደሪያ ናት፡፡ እግዚአብሔር የመሠረታት፣ የቀደሳትና የዋጃት፣ ሐዋርያት፣ ነቢያትና ቅዱሳን አበው የሰበኳትና ያጸኗት ቤት ናት፤ ለሰውም በረከተ ሥጋንና በረከተ ነፍስን ታድላለች፡፡

ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ

በሕይወት ሳልለው

በሸዋ ቡልጋ ክፍለ ሀገር ጌዬ በተባለ አካባቢ የተወለደችው ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ አባቷ ደረሳኒ እና እናቷ ዕሌኒ በእግዚአብሔር ፊት የታመኑ ሰዎች ነበሩ፡፡ ልጃቸውን የቤተክርስቲያን ሥርዓት፤ የብሉይና የሐዲስ ኪዳንን መጻሕፍት በማስተማር አሳደጓት፡፡ ዕድሜዋ ለአቅመ ሔዋን ሲደርስ ወላጆቿ የኢየሱስ ሞዓ ልጅ የሆነውን ሠምረ ጊዮርጊስን አጋቧት፤ ዐሥር ወንዶችና ሁለት ሴቶች ልጆችን ወለደች፤ እርሷም ልጆቿን በሥርዓትና በሕገ እግዚአብሔር አሳደገቻቸው፡፡

በዚያ ዘመን የነበረው ንጉሥ ዓፄ ገብረ መስቀል ደግ ሰው ነበር፡፡ በአንድ ወቅት ንጉሡ ስለ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ቁንጅናና ደግነት በሰማበት ወቅት በግዛቱ ከተደነቁት ፻፸፬ ሴቶች መካከል አንዷ ስለነበረች ስለእርሷ ዝና አወቀ፡፡ ንጉሡም ያገለግሏት ዘንድ ፪፻፸፪ ያህል ብላቴናዎችን ላከላት፡፡ ነገር ግን ይህ ውዳሴ ከንቱ እንዳይሆን ወደ እግዚአብሔር ባመለከተች ጊዜ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል በራዕይ ተገልጾላት፡፡ «ሰላም ላንቺ ይሁን የተወደድሽ ክርስቶስ ሠምራ ሆይ፤ የእግዚአብሔር ቸርነት የሆነውን የሰማይ ኅብስትም ተመገቢ» ብሎም መገባት፡፡ በውስጧም መንፈስ ቅዱስ መላባት፤ ፈጣሪዋን አመሰገነች፤ ከንጉሡ የተላኩላትንም አገልጋዮች አስተባብራ ቅዱስ ሚካኤል እንዳዘዛት በስሙ ቤተክርስቲያን አሠራች፡፡ የመልአኩን የቃል ኪዳን ታቦት ወደ ቤተ መቅደስ በማስገባት በዚያ ስታገለግልና ስታስገለግል ኖረች፡፡

ከዕለታት በአንዱ ቀን ግን ከአገልጋዮቿ አንዷ ላይ ርኩስ መንፈስ አደረ፤ አልታዘዝም ማለትም ጀመረች፡፡ ይህን ጊዜ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ደጋግማ መከረቻት፤ ያቺ ብላቴና ግን ልትመከር አልቻለችም፤ በዚህም ሳቢያ ክፉኛ ብታዝንባት ብላቴናዋ ሞተች፡፡ እጅጉን ያዘነችው እናታችን «ይህማ የነፍስ ግድያ ይሆንብኛል» ብላ አምርራ አለቀሰች፤ ወደ እግዚአብሔር በጸለየች ጊዜ ፈጣሪ አገልጋይቱን ከሞት አስነሳላት፡፡ ውስጧም በሐሴት ተሞላ፤ እንዲህም አለች «በዓለማዊ ሕይወት ውስጥ ስኖር ይህን ተአምር ካደረገልኝ በምናኔ ሕይወት ብኖር ደግሞ ምን ያህል ድንቅ ሥራ ያደርግልኛል፤» ብላ ባለቤቷንና ልጆቿን እንዲሁም ወላጆቿን ትታ መነኮሰች፡፡ ነገር ግን የመጨረሻው ልጇን ወደ ደብረ ሊባኖስ ገዳም በገባች ጊዜ አብራ ይዛው ሔደች፡፡ የአካባቢው ሰዎች ከሩቅ ቦታ እንደመጣች አውቀው አስጠጓት፤ እርሷም ልጇን በዚያው አስቀመጣ በገዳሙ ውስጥ በጸሎት፤ በጾምና በስግደት ስትተጋም ቆየች፡፡ ልጇ ግን እናቱን ባጣ ጊዜ አለቀሰ፤ተራበም፡፡ በደጃፉ ስታለፍ የነበረች አንዲት ሴት ልጁን ተጠግታ ልታነሳው ብትሞክር ቅዱስ ሚካኤል ፈጥኖ ደርሶ ነጥቆ ወሰደው፤ ወደ ገነትም አስገባው፡፡ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራም ወደ ልጇ በተመለሰች ጊዜ ሞቶ አገኘችው፡፡ መሪር ኃዘንም አዘነች፤ ይህን ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ተገልጾ ልጇ በገነት እንዳለ ነግሮ አጽናናት፡፡ ወደ ጣና ባሕርም መርቶ ወሰዳት፤ በዚያም ለ፲፪ ዓመት በባሕር ውስጥ ገብታ ሰውነቷ ተበሳስቶ ዓሣዎች በውስጧ እስኪያልፉ ድረስ ቆማ ጸለየች፤ ጌታችን  ኢየሱስ ክርስቶስም ተገልጾ ቃልኪዳን ሰጣት፤ ፲ አክሊላትም ወረዱላት፡፡ በጸሎትና በስግደትም መትጋት በቀጠለችበት ወቅት ቅዱስ ሚካኤልን፣ ቅዱስ ገብርኤልን፣ ቅዱስ ሩፋኤልንና እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያምም ረዳት እንዲሆኗት ጌታችን ፈቀደላት።

እናታችን ክርስቶስ ሠምራ ደግና ርኅሩኅ ነበረችና ጌታን እንዲህ ብላ ለመነችው «አቤቱ ፈጣሪዬ እኔን ባሪያህን ከክፉ ነገር ሁሉ ሠውረኸኛልና ዲያብሎስን ትምረው ዘንድ እለምንሃለሁ፡፡ ይኸውም ስለ አዳምና ስለ ልጆቹ በጠቅላላውም ስለ ሰብአ ዓለም ሥጋቸው ሥጋዬ ስለሆነ እንዳያስታቸው ክፉ ሥራ እንዳያሠራቸው ብዬ ነው ማርልኝ ማለቴ» አለችው፡፡ ጌታችንም «ወዳጄ ክርስቶስ ሠምራ ሆይ ዕፁብ ድንቅ ልመና ለመንሽኝ! ሌሎች በኋላሽም የነበሩ በፊትሽም የሚመጡ ያልለመኑትን ልመና ለመንሽኝ» አላት፡፡ ቅዱስ ሚካኤልንም ወደ ዲያብሎስ እንዲወስዳት አዘዘው፡፡

ሲኦል ሲደርሱ ምሕረትን የሚሻ ከሆነ እንድትጠይቀው ቅዱስ ሚካኤል ባዘዛት ጊዜ፤ «ሳጥናኤል» ብላ ጠራቸው፡፡ ዲያብሎስም መልሶ ሳጥናኤል ብሎ የጠራኝ ማን ነው? አለ፡፡ እርሷም «እኔ ነኝ» አለችው፡፡ ወደ እኔ ለምን መጣሽ ሲላት  «ከፈጣሪህ ጋር አስታርቅህ ብየ» አለችው፡፡ እርሱም አንቺን ከቤትሽ ከንብረትሽ ሳለሽ አስትሻለሁ ብየ ብመጣ ያጣሁሽ ሰው እኔን ልታስታርቂኝ መጣሽ? ግን ይህን ያደረገ ያ የቀድሞው ጠላቴ ሚካኤል ነው፤ ሲጻረረኝ የሚኖር ከክብሬም ያወረደኝ እሱ ነው እንጂ አንቺ ምን ጉልበት አለሽ ብሎ እጇን ይዞ ወደ ሲኦል ወረወራት፡፡

በዚያች ቅጽበት ቅዱስ ሚካኤል ሲኦልን በሰይፉ መታው፤ ተከፈተም፤ በውስጡም ብዙ ነፍሳት እርስ በርስ ሲነባበሩ አየች፤ ነፍሷም ታበራ ስለነበር ፲ ሺህ ያህል ነፍሳት መጥተው በላይዋ ሰፈሩባት፤ ከሲኦልም ይዛቸው ወጣች፤ እነዚያን ነፍሳት የማረላትንም ፈጣሪዋን አመሰገነች፡፡

ጌታችን ኢየሱስም ለእናታችን ክርስቶስ ሠምራ ማረፊያዋ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በስተቀኝ እንደሚሆን እና ስሟም ከእንግዲህ በኋላ በትረ ማርያም ተብሎ እንደሚጠራ ነገራት፡፡ እመቤታችንም ተገልጻ «ወዳጄ ክርስቶስ ሠምራ ሆይ፤ አንቺን የወለደች ማሕፀን የተባረከች ናት፤ አንቺንም አጥብተው ያሳደጉ ጡቶች የተባረኩ ናቸው፡፡ አንቺንም ያዩ ዐይኖች የተባረኩ የተቀደሱ ናቸው፤ አንቺንም የሚያመሰግኑ ንዑዳን ክቡራን ናቸው፤ያንቺን ገድል የሚሰሙ፤ የሚያሰሙ የተባረኩ ናቸው»፤ አለቻት፡፡

ከዚህ በኋላ ሥጋዋ ከነፍሷ ተዋሕዶ ወደ መሬት ተመለሰች፤ በቁመቷ ልክ ጉድጓድ አስቆፍራ፤ በዙሪያዋ ጦሮችን አስተከለች፤ ይህም ወደፊትና ወደኋላ በምትልበት ጊዜ እንዲወጋት ነበር፤ ለ፲፪ ዓመትም እየሰገደች ኖረች፡፡

ጌታችንም እንዲህ አላት፤«አንቺን የሚወዱ፤ ስምሽን የሚጠሩ፤ ዝክርሽን የዘከሩና በዓልሽን ያከበሩ እስከ ፲፪ ትውልድ እምርልሻለሁ»፡፡ በመጨረሻም ነሐሴ ፳፬ ቀን ነፍሷ ከሥጋዋ ተለይታ መላእክት አሳረጓት፤ የቅድስት ክርስቶስ ሠምራ የከበረ ዐፅም ጌዬ የተባለ ገዳም ውስጥ ተቀምጧል፤ ይህም ገዳም እርሷን መዘከርና መማጸን ለሚሹ ምእመናን የተሠራ ነው፡፡

ምንጭ፡- ገድለ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ፤ ነገረ ቅዱሳን ቁጥር ፪ እና ዝክረ ቅዱሳን