‹‹ለችግረኛና ለምስኪን የሚያስቡ ብፁዓን ናቸው›› (መዝ. ፵፥፩)
ሰዎች በቅን ልቡና ተነሣሥተው ችግረኞችን መርዳት ይችሉ ዘንድ እነማንን መርዳት እንዳለባቸው ማወቅ ተገቢ ይሆናል፡፡ ምክንያቱም ችግረኞችን ለይተን ማወቅ ካልቻልን የሚለምኑ ሁሉ ችግረኞች እየመሰሉን ርዳታ ለሚያስፈልጋቸው ነዳያን ተገቢውን ርዳታ ላናደርግላቸው እንችላለን፡፡ ለዚህም መስፈርት አድርገን የምናስቀምጣቸው መሠረታዊ ነገሮች ምግብ፣ አልባሳትና መጠለያ ያልተሟላላቸውን ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የጤና እክል ያለባቸው፣ በደዌ ዳኛ በአልጋ ቁራኛ የተያዙና ባለባቸው ችግር የተነሣ ሠርተው መብላት ያልቻሉ፣ አልባሽ አጉራሽ ቤተሰብም ሆነ ዘመድ የሌላቸውንም ችግረኞች እንላቸዋለን፡፡ በተጓዳኝ ረዳት ያጡ፣ ጠዋሪና ቀባሪ የሌላቸው አረጋውያን፣ ወላጅ አልባ ሕፃናት፣ በተለያዩ ምክንያቶች ቤት ንብረታቸውን አጥተው ከቀዬያቸው የተፈናቀሉትንም መርዳት ያስፈልጋል፡፡