ዘመነ ክረምት – የመጨረሻ ክፍል

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መስከረም ፲፮ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ተከታታዮች! በክፍል ስምንት ዝግጅታችን ስድስተኛውን የክረምት ንዑስ ክፍል (ዘመነ ፍሬን) በሚመለከት ወቅታዊ ትምህርት ማቅረባችን ይታወሳል፡፡ በዛሬው የመጨረሻ ክፍል ዝግጅታችን ደግሞ ሰባተኛውን ክፍለ ክረምት (ፀአተ ክረምትን ወይም ዘመነ መስቀልን) የሚመለከት ትምህርት ይዘን ቀርበናል፡፡ ትምህርቱን እንድትከታተሉ መንፈሳዊ ግብዣችንን አስቀድመናል፡፡ መልካም የንባብ ጊዜ ይኹንላችሁ!

፯. ፀአተ ክረምት (ዘመነ መስቀል)

ከመስከረም ፲፮ – ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ሰባተኛው የክረምት ክፍለ ጊዜ ፀአተ ክረምት ወይም ዘመነ መስቀል በመባል የሚታወቅ ሲኾን ይኸውም የክረምት መውጣት እና በአተ መጸው (የመጸው መግባት) የሚሰበክበት ወቅት ነው፡፡ የፀአተ ክረምት መጨረሻ የሚኾነውም መስከረም ፳፭ ቀን ነው፡፡ ‹ፀአተ ክረምት› የሚለው የግእዝ ቃላት ጥምረት ‹የክረምት መውጣት› የሚል ትርጕም አለው፡፡ የክረምት መውጣት ሲባል ለዘመነ ክረምት የተሰጠው ጊዜ በዘመነ መጸው መተካቱን ለማመልከት እንጂ ክረምት ተመልሶ አይመጣም ለማለት አይደለም፡፡ የሰው ልጅ ምድራዊ ሕይወት እስከሚያበቃበት እስከ ኅልፈተ ዓለም ድረስ የወቅቶች መፈራረቅም አብሮ ይቀጥላልና፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትም ይህንን የወቅቶች መፈራረቅ ለመግለጽ ነው ‹‹መግባት፣ መውጣት›› እያሉ በክፍል በክፍል የሚያስቀምጧቸው፡፡

ጠቢቡ ሰሎሞን ‹‹እስመ ናሁ ክረምት ኀለፈ ወዝናም ገብአ ድኅሬሁ ጽጌ አስተርአየ በውስተ ምድርነ ጊዜ ገሚድ በጽሐ ቃለ ማዕነቅ ተሰምዐ በምድርነ በለስ አውጽአ ሠርጸ አውያን ጸገዩ ወወሀቡ መዓዛ፤ እነሆ ክረምት ዐለፈ፤ ዝናቡም ዐልፎ ሔደ፡፡ አበባ በምድር ላይ ታየ፤ የመከርም ጊዜ ደረሰ፡፡ የቊርዬውም ቃል በምድራችን ተሰማ፡፡ በለሱ ጐመራ፤ ወይኖችም አበቡ፤ መዓዛቸውንም ሰጡ፤›› (መኃ. ፪፥፲፩-፲፫) በማለት እንደ ተናገረው አሁን የክረምቱ ጊዜ አብቅቶ ሌላ ወቅት ዘመነ መጸው ተተክቷል፡፡ መጭው ዘመን የተስፋ፣ የንስሐና የጽድቅ ወቅት እንዲኾንልን እግዚአብሔርን ከፊት ለፊታችን ማስቀደም ይኖርብናል፡፡ እርሱ ከቀደመ መሰናክሎቹን ለማለፍ፣ ፈተናዎችንም ለመወጣት ምቹ ኹኔታዎችን እናገኛለንና፡፡ ክረምቱ አልፎ መጸው ሲተካ ምድር ባገኘችው ዝናም አማካይነት የበቀሉ ዕፀዋት በአበባና በፍሬ ይደምቃሉ፡፡ ምእመናንም በተማርነው ቃለ እግዚአብሔር ለውጥ በማምጣት እንደ ዕፀዋት በመንፈሳዊ ሕይወታችን አፍርተን ክርስቲያናዊ ፍሬ ማስገኘት ይኖርብናል፡፡ በዚህ ፍሬያችን ዘለዓለማዊውን የእግዚአብሔር መንግሥት ለመውረስ እንችላለንና፡፡

አንድ ክፍለ ጊዜ (ወቅት) ሲያልፍ ሌላ ክፍለ ጊዜ ይተካል፡፡ ‹‹ሲሞት ሲተካ፣ ሲፈጭ ሲቦካ›› እንደሚባለው የሰው ልጅ ሕይወትም እንደዚሁ ነው፡፡ አንደኛው ሲሞት ሌላኛው ይወለዳል፤ አንደኛው ሲወለድ ሌላኛው ይሞታል፡፡ ወቅቶችም የጊዜ ዑደት መንገዶች እንደ መኾናቸው ለሰው ልጅ ምቾት እንጂ ለራሳቸው ጥቅም የተዘጋጁ ሕያዋን ፍጥረታት አይደሉም፡፡ በመኾኑም ራሳቸውን እየደጋገሙ ይመላለሳሉ፤ የሰው ልጅ ግን አምሳሉን ይተካል እንጂ ራሱ ዳግመኛ ተመልሶ አይመጣም፡፡ እንግዲህ ክርስቶስ ለፍርድ ሲመጣ እንዳናፍር ዳግም በማናገኛት በዚህች ምድራዊ ሕይወታችን የማያልፍ ክርስቲያናዊ ምግባር ሠርተን ማለፍ ይጠበቅብናል፡፡ ከሞት በኋላ ዘለዓለማዊ ፍርድ እንጂ ንስሐ የለምና፡፡

መንፈሳዊ ዓላማችን ይሳካልን ዘንድም እግዚአብሔርን በጸሎት እንጠይቀው፡፡ እንደዚህ እያልን፤ ‹‹ድኅረ ኀለፈ ክረምት ወገብአ ዝናም፤ ዘአርአይከ እግዚኦ ጽጌያተ ገዳም፤ አፈወ ሃይማኖት ነዓልድ ወፍሬ ምግባር ጥዑም፤ አትግሀነ ለስብሐቲከ ከመ ትጋሆሙ አዳም፤ ለጽብስት ንህብ ወነአስ ቃህም፡፡›› ትርጕሙም፡- ‹‹ክረምት ካለፈ፣ ዝናምም ወደ ቦታው ከተመለሰ በኋላ የዱር አበቦችን ያሳየህ አቤቱ እግዚአብሔር ሆይ! የሃይማኖት ሽቱን እናስገኝና የሚጣፍጥ የምግባር ፍሬን እናፈራ ዘንድ ተወዳጅ እንደ ኾነው የታታሪዋ ንብና የብልሃተኛዋ ገብረ ጕንዳን ትጋት እኛንም ለምስጋናህ አትጋን›› ማለት ነው (መጽሐፈ ስንክሳር፣ የመስከረም ፳፭ ቀን አርኬ)፡፡

በተጨማሪም በዚህ ወቅት (ከመስከረም ፲፮ – ፳፭ ቀን ድረስ ባለው ክፍለ ክረምት) ነገረ መስቀሉን የሚመለከት ትምህርት በቤተ ክርስቲያናችን በሰፊው ይነገራል፡፡ ማለትም ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጅ ድኅነት ሲል በፈቃዱ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ስለ መሞቱ፣ በሞቱም ዓለምን ስለ ማዳኑ፣ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ያፈሰሰሰበት ዕፀ መስቅሉ የተቀደሰ ስለ መኾኑ ከሌሎች ጊዜያት በላይ በስፋት የሚነገረውና ትምህርት የሚሰጠው በዚህ ወቅት ነው፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም በአይሁድ ቅናት በጎልጎታ ለ፫፻ ዓመታት ያህል ተቀብሮ የቆየው የጌታችን ዕፀ መስቀልን ለማውጣት በንግሥት ዕሌኒ አማካይነት ቍፋሮ መጀመሩ፣ መስቀሉ ከወጣ በኋላም በዐፄ ዳዊትና በልጃቸው በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ጥረት ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ በግሸን ደብረ ከርቤ መቀመጡ የሚዘከረው በእነዚህ ዐሥር የፀአተ ክረምት ዕለታት ውስጥ ነው፡፡ እኛ ምእመናን ይህንን የመስቀሉን ነገር በልቡናችን ይዘን በክርስትናችን ምክንያት የሚገጥመንን ልዩ ልዩ ዓይነት ፈተና በትዕግሥት ማሳለፍ ይጠበቅብናል፡፡

ማጠቃለያ

ትምህርታችንን ለማጠቃለል ያህል ዘመነ ክረምት ስለ ሥነ ፍጥረት ዘርዘር ባለ መልኩ የሚነገርበት፤ ፍጡርን ከፈጣሪ መናን (ምግብን) ከተመጋቢ ለይቶ የሚያሳይ እና የሚያሳውቅ ዘመን ነው፡፡ በዚህ ወቅት የውኃ ባሕርይ ይሠለጥናል፤ ውኃ አፈርን ያጥባል፤ እሳትን ያጠፋል፡፡ ኾኖም ግን ውኃ በብሩህነቱ ከእሳት፤ በቀዝቃዛነቱ ከነፋስ፤ በእርጥብነቱ ከመሬት ጋር ተስማምቶ ከሦስቱ ባሕርያት ጋር ይኖራል፡፡ ይህን ምሥጢር ከሕይወታችን ጋር አያይዘን ስንመለከተው ዘመነ ክረምት የክርስትና ምሳሌ ነው፡፡ በክረምት ወቅት ገበሬው ብርዱንና ዝናሙን ሳይሰቀቅ ለሥራ ይሰማራል፤ በበጋው የእጁን ፍሬ ያገኝ ዘንድ የክረምቱን መከራ ይታገሣል፡፡ ይህም ምእመናን በሰማያዊው ዓለም የምናገኘውን ተድላና ደስታ በማሰብ በምድር ቆይታችን ወቅት የሚደርስብንን ልዩ ልዩ መከራ በትዕግሥት ማሳለፍ እንደሚገባን ያስገነዝባል፡፡

ዘመነ ክረምት ዕፀዋቱ በስብሰው ከበቀሉ፣ ካበቡና ካፈሩ በኋላ የሚጠቅሙት በሪቅ፣ በጎተራ እንደሚሰበሰቡ፤ እንክርዳዶቹ ደግሞ በእሳት እንደሚቃጠሉ ዅሉ እኛም ተወልደን፣ አድገን፣ ዘራችንን ተክተን እንደምንኖር፤ ዕድሜያችን ሲያበቃም እንደምንሞት፤ ሞተንም እንደምንነሣና መልካም ሥራ ከሠራን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እንደምንገባ፤ በኀጢአት ከኖርን ደግሞ በገሃነመ እሳት እንደምንጣል የምንማርበት ወቅት ነው፡፡ በመኾኑም ሰይጣን በሚያዘንበው የኀጢአት ማዕበል እንዳንወሰድና በኋላም በጥልቁ የእሳት ባሕር እንዳንጣል ዅላችንም ቅዱሳት መጻሕፍትና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያዘጋጁልንን የቃለ እግዚአብሔር ዘር በእርሻ ልቡናችን በመዝራት (በመጻፍ) እንደየዓቅማችን አብበን፣ ያማረ ፍሬ አፍርተን መንግሥቱን ለመውረስ መዘጋጀት ይኖርብናል፡፡ ይህንን እንድናደርግም የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእናታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነትና የቅዱሳኑ ዅሉ ተራዳኢነት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ዘመነ ክረምት – ክፍል ስምንት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መስከረም ፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

፮. ዘመነ ፍሬ

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ተከታታዮች! በክፍል ሰባት ዝግጅታችን አምስተኛውን የክረምት ንዑስ ክፍል (ቅዱስ ዮሐንስን) የሚመለከት ትምህርት ማቅረባችን ይታወሳል፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን ደግሞ ስድስተኛውን ክፍለ ክረምት (ዘመነ ፍሬን) የሚመለከት ትምህርት ይዘን ቀርበናል፡፡ እንድትከታተሉን መንፈሳዊ ግብዣችንን አስቀድመናል፡፡ መልካም የንባብ ጊዜ ይኹንላችሁ!

ከመስከረም ፱ – ፲፭ ቀን ያለው ስድስተኛው ክፍለ ክረምት ‹ፍሬ› ይባላል፡፡ ‹ዘመነ ፍሬ› ደግሞ ‹የፍሬ ወቅት፣ የፍሬ ዘመን፣ የፍሬ ጊዜ› ማለት ሲኾን ይኸውም ልዩ ልዩ አዝርዕት በቅለው፣ አድገው፣ አብበው ለፍሬ የሚደርሱበት፤ የሰው ልጅ፣ እንስሳትና አራዊትም ጭምር የዕፀዋቱን ፍሬ (እሸት) የሚመገቡበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ወቅት በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚቀርቡ ምንባባትና ትምህርቶችም ይህንኑ ምሥጢር የሚዳስሱ ናቸው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ምድርን ከፈጠረ በኋላ በጥፍር የሚላጡትን (ሎሚ፣ ሙዝ፣ ትርንጎ፣ ወዘተ)፤ በማጭድ የሚታጨዱትን (ስንዴ፣ ጤፍ፣ ገብስ፣ ወዘተ)፤ በምሳር የሚቈረጡትን (ወይራ፣ ዋርካ፣ ዋንዛ፣ ዝግባ፣ ወዘተ)፤ የገነት ዕፀዋትን ፈጥሯል፡፡ እነዚህም በራሳቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ስንዴ፣ገብስ፣ ጤፍ፣ ወዘተ)፤ በጎድናቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ማሽላ፣ በቆሎ፣ ባቄላ፣ ወዘተ)፤ በውስጣቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ዱባ፣ ቅል፣ ወዘተ)፤ በሥራቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ሽንኩርት፣ ቀይ ሥር፣ ካሮት፣ ድንች፣ ወዘተ) ተብለው በአራት ይመደባሉ (ምንጭ፡- ትርጓሜ ኦሪት ዘፍጥረት ፩፥፮-፲፫)፡፡

ተፈጥሯቸውም እንደ ሰው ከአራቱ ባሕርያት ነው፡፡ ከነፋስ በመፈጠራቸው በነፋስ ያብባሉ፤ ያፈራሉ፡፡ ከእሳት በመፈጠራቸው እርስበርሳቸው ሲፋተጉ እሳት ያስገኛሉ (አንዳንዶቹ)፡፡ ከውኃ በመፈጠራቸው ፈሳሽ ያወጣሉ፡፡ ከአፈር በመፈጠራቸው ሲቈረጡ በስብሰው ወደ አፈርነት ይቀየራሉ፡፡ እኛ የሰው ልጆችም በተፈጥሯችን (በባሕርያችን) ከዕፀዋት ጋር እንመሳሰላለን፡፡ በነፋስ ባሕርያችን ፍጥነት፤ በእሳት ባሕርያችን ቍጣ፤ በውኃ ባሕርያችን መረጋጋት፤ በመሬት ባሕርያችን ትዕግሥት ወይም ሞት ይስማማናልና፡፡ በሌላ በኩል የአዘርዕት ከበሰበሱ በኋላ መብቀልና ማፍራት የትንሣኤ ሙታን ምሳሌ ነው፡፡ አዝርዕት ከበሰበሱ በኋላ ፍሬ እንደሚያስገኙ ዅሉ ሰውም ከሞተ በኋላ ተነሥቶ እንደ ሥራው መጠን ዋጋውን ይቀበላልና፡፡ ይህንን ቅዱስ ጳውሎስ በምሳሌ አስተምሮናል፡፡ እንዲህ ሲል፤ ‹‹… የሙታን ትንሣኤ ደግሞ እንዲሁ ነው፡፡ በመበስበስ ይዘራል፤ ባለ መበስበስ ይነሣል፡፡ በውርደት ይዘራል፤ በክብር ይነሣል፡፡ በድካም ይዘራል፤ በኃይል ይነሣል፡፡ ፍጥረታዊ አካል ይዘራል፤ መንፈሳዊ አካል ይነሣል …›› (፩ኛ ቆሮ. ፲፭፥፵፪-፵፬)፡፡

አዝርዕት ተዘርተው ከበሰበሱ በኋላ በቅለው፣ አብበው በራሳቸው፣ በጎድናቸው፣ በውስጣቸውና በሥራቸው እንደሚያፈሩ ዅሉ እኛም በራስ እንደ ማፍራት ፈሪሃ እግዚአብሔርን፤ በጎድን እንደ ማፍራት እርስበርስ መደጋገፍንና መተሳሰብን፤ በውስጥ እንደ ማፍራት ንጽሕናን፤ በሥር እንደ ማፍራት ትሕትናን ገንዘብ ማድረግን ከዕፀዋትና ከአዝርዕት መማር ይገባናል፡፡ እንደዚሁም ዕፀዋት ሠላሳ፣ ስድሳ፣ መቶና ከዚያ በላይ መልካም ፍሬ እንደሚያፈሩ በመልካሟ መሬት በክርስትና የተዘራን እኛ ክርስቲያኖችም ዘር የተባለውን የእግዚአብሔርን ቃል በሚገባ ተምረን ከወጣኒነት ወደ ማእከላዊነት፤ ከማእከላዊነት ወደ ፍጹምነት በሚያደርስ የጽድቅ ሥራ በመትጋት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ መፋጠን ይኖርብናል (ማቴ. ፲፫፥፳፫)፡፡

ዕፀዋት የሚሰጡት ፍሬ እንደየማፍራት ዓቅማቸው ይለያያል፤ ፍሬ የማያፈሩ፣ ጥቂት ፍሬ የሚያፈሩ፣ ብዙ ፍሬ የሚያፈሩ ዕፀዋት ይገኛሉ፡፡ እንደዚሁ ኹሉ ምእመናንም በክርስትና ሕይወታችን የሚኖረን በጎ ምግባር የአንዳችን ከአንዳችን ይለያል፡፡ ፍሬ የክርስቲያናዊ ምግባር እንደዚሁም የሰማያዊው ዋጋ ምሳሌ ነውና፡፡ በክርስትና ሕይወት ያለምንም በጎ ምግባር የምንኖር ኀጥአን ብዙዎች የመኾናችንን፤ እንደዚሁም ጥቂት በጎ ምግባር ያላቸው ምእመናን የመኖራቸውን ያህል በአንጻሩ ደግሞ በጽድቅ ላይ ጽድቅ፣ በመልካም ሥራ ላይ መልካም ሥራን የሚፈጽሙ፤ ከጽድቅ ሥራ ባሻገር በትሩፋት ተግባር ዘወትር ጸንተው የሚኖሩ አባቶችና እናቶችም ጥቂቶች አይደሉም፡፡ ይህን ዓይነት የክርስቲያናዊ ሕይወት ልዩነት ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹በጥቂት የሚዘራ በጥቂት ደግሞ ያጭዳል፤ በበረከትም የሚዘራ በበረከት ደግሞ ያጭዳል … ለዘሪ ዘርን ለመብላትም እንጀራን በብዙ የሚሰጥ እርሱም የምትዘሩትን ዘር ይሰጣችኋል፤ ያበረክትላችሁማል፡፡ የጽድቃችሁንም ፍሬ ያሳድጋል›› በማለት ይገልጸዋል (፪ኛ ቆሮ. ፱፥፮-፲)፡፡ ገበሬ በዘራው መጠን ሰብሉን እንዲሰበስብ ‹‹ለዂሉም እንደየሥራው ዋጋውን ትከፍለዋለህ›› ተብሎ እንደ ተጻፈው ክርስቲያንም በሠራው መጠን ዋጋውን ያገኛልና በጸጋ ላይ ጸጋን፣ በበረከት ላይ በረከትን ከእግዚአብሔር ዘንድ ይጨመርልን ዘንድ ዂላችንም መልካም ሥራን በብዛት ልንፈጽም ይገባናል፡፡ ‹‹… እንግዲህ ወንድሞች ሆይ ጌታ እስኪመጣ ድረስ ታገሡ፡፡ እነሆ ገበሬው የፊተኛውንና የኋለኛውን ዝናብ እስኪቀበል ድረስ እርሱን እየታገሠ የከበረውን የመሬት ፍሬ ይጠብቃል፡፡ እናንተ ደግሞ ታገሡ፤ ልባችሁንም አጽኑ፡፡ የጌታ መምጣት ቀርቧልና›› እንዳለን ሐዋርያው (ያዕ. ፭፥፯-፰)፡፡

ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ‹‹ምድርኒ ወሀበት ፍሬሃ፤ ምድርም ፍሬዋን ሰጠች›› (መዝ. ፷፮፥፮፤ ፹፬፥፲፪) የሚለውን የዳዊት መዝሙርና ሌሎችንም ተመሳሳይ ኃይለ ቃላት ሲተረጕሙ ምድር በኢየሩሳሌም፣ በቤተ ክርስቲያን፣ በምእመናን፣ በእመቤታችን፤ ፍሬ ደግሞ በቃለ እግዚአብሔር (በሕገ እግዚአብሔር)፣ በአምልኮተ እግዚአብሔር፣ እንደዚሁም በጌታችን አምላካችን መድኂታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሚመሰል ያስተምራሉ፡፡ በዚህ መሠረት ‹‹ምድርኒ ወሀበት ፍሬሃ፤ ምድርም ፍሬዋን ሰጠች›› በሚለው ኃይለ ቃል ምድር የተባለች ኢየሩሳሌም የዘሩባትን እንደምታበቅል፤ የተከሉባትን እንደምታጸድቅ፤ አንድም ይህቺ ዓለም ፍሬን፣ አምልኮተ እግዚአብሔርን እንደምታቀርብ፤ ቤተ ክርስቲያን ወይም ምእመናን እግዚአብሔርን ሲያመልኩ እንደሚኖሩ፤ ከዚሁ ዂሉ ጋርም ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እንደ ተወለደ የሚያስረዳ ምሥጢር አለው፡፡ ‹‹ምድርኒ ወሀበት ፍሬሃ፤ ምድርም ፍሬዋን ሰጠች›› – ምድር ከተባለች ከቅድስት ድንግል ማርያም ፍሬ የተባለው ክርስቶስ መገኘቱን ለማጠየቅም ቅዱስ ገብርኤል በሉቃስ ወንጌል የተናገረው ቃል ማስረጃ ነው (ሉቃ. ፩፥፳፰)፡፡ እኛም የመልአኩን ቃል መሠረት አድርገን በዘወትር ጸሎታችን ‹‹ቡርክት አንቲ እምአንስት ወቡሩክ ፍሬ ከርሥኪ፤ አንቺ ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ፤ የማኅፀንሽ ፍሬም የተባረከ ነው›› እያልን ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እና ለልጇ ኢየሱስ ክርስቶስ ውዳሴ እናቀርባለን፡፡

በማቴዎስ ወንጌል ፲፫፥፩-፳፫ ተጽፎ እንደምናገኘው ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የክርስትና ሕይወትን ከዘርና ፍሬ ጋር በማመሳሰል አስተምሯል፡፡ ይኸውም አንድ ገበሬ ዘር ሲዘራ በመንገድ ዳር የወደቀው ዘር ከመብቀሉ በፊት በወፎች እንደ ተበላ፤ በጭንጫ ላይ የተጣለውም ወዲያውኑ ቢበቅልም ነገር ግን ጠንካራ ሥር ስለማይኖረው በፀሐይ ብርሃን እንደ ጠወለገ፤ በእሾኽ መካከል የወደቀው ደግሞ ሲበቅል በእሾኽ እንደ ታነቀ፤ ከዂሉም በተለየ መልኩ በመልካም መሬት ላይ የተጣለው ዘር ግን አድጎ መቶ፣ ስድሳ፣ ሠላሳ ፍሬ እንደ ሰጠ የሚያስረዳ ነው፡፡ ይህም ምሳሌ አለው፡፡ ጌታችን ለደቀ መዛሙርቱ እንደ ተረጐመው በመንገድ ዳር የተዘራው ዘር የእግዚአብሔርን ቃል ሰምቶ የማያስተውል ክርስቲያን ምሳሌ ነው፤ ሙሉ እምነት ስለማይኖረው በመከራው ጊዜ አጋንንት ይነጥቁታልና፡፡ በጭንጫ ላይ የተዘራው ደግሞ ቃሉን ሰምቶ ወዲያው በደስታ የሚቀበል፣ ነገር ግን ተግባራዊ የማያደርግ ክርስቲያን ምሳሌ ነው፡፡ ይህ ምእመን በጠንካራ እምነት ላይ የጸና አይደለምና በሃይማኖቱ ምክንያት መከራ ወይም ስደት በደረሰበት ጊዜ ፈጥኖ ይሰናከላል፡፡ በእሾኽ መካከል የተዘራውም ቃሉን የሚሰማ ነገር ግን በዚህ ዓለም ዐሳብና ባለጠግነት ተታሎ ቃሉን የማይተገብር ክርስቲያን ምሳሌ ነው፡፡

በመልካም መሬት የተዘራው ደግሞ ቃሉን ሰምቶ የሚተገብር ክርስቲያን ምሳሌ፡፡ እንደዚህ ዓይነት ምእመን በተማረው ትምህርት ጸንቶ ይኖራል፤ መልካም ሥራም ይሠራል፡፡ በመልካም መሬት የተዘራው ዘር ስለ አንዱ ፋንታ መቶ፣ ስድሳ፣ ሠላሳ እንደሚያፈራ ዅሉ በክርስቲያናዊ ግብር ጸንቶ የሚኖር ምእመንም ሥራውን በሦስት መንገድ ማለትም በወጣኒነት፣ በማእከላዊነትና በፍጹምነት ደረጃ እንደሚወጣ፤ ዋጋውንም በሥራው መጠን እንደሚያገኝ የሚያስረዳ ነው፡፡ አንድም ባለ መቶ ፍሬ የሰማዕታት፤ ባለ ስድሳ የመነኮሳት፤ ባለ ሠላሳ በሕግ ተወስነው በዓለም የሚኖሩ ምእመናን ምሳሌ ነው፡፡ በተመሳሳይ ምሥጢር ዂሉም የፍሬ መጠን በዅሉም ጾታ ምእመናን ሕይወት ውስጥ እንደሚስተዋል ሊቃውንት ይተረጕማሉ፡፡ ስለዚህም በሰማዕትነትም፣ በምንኵስናም፣ በዓለማዊ ሕይወትም ውስጥ የሚኖሩ ምእመናን መልካም ግብራቸው እጅግ የበዛ ከኾነ በባለ መቶ ፍሬ፤ መካከለኛ ከኾነ በባለ ስድሳ፤ ከዚህ ዝቅ ያለ ከኾነ ደግሞ በባለ ሠላሳ ፍሬ ይመሰላል (ምንጭ፡- ትርጓሜ ወንጌለ ማቴዎስ)፡፡

ከዚሁ ዂሉ ጋርም ዕፀዋት ለመጠለያነት የማይጠቅሙ እንደዚሁም ለምግብነት ወይም ደግሞ ለመድኀኒትነትና ለሌላም ልዩ ልዩ አገልግሎት የሚጠቅም ፍሬ የማያስገኙ ከኾነ ተቈርጠው ይጣላሉ፡፡ ምእመናንም ‹ክርስቲያን› ተብለን እየተጠራን ያለ ምንም በጎ ምግባርና መንፈሳዊ ሕይወት ከኖርን ከእግዚአብሔር መንግሥት ውጪ እንኾናለን፡፡ ከኀጢአት ካልተለየን በምድር መቅሠፍት ይታዘዝብናል፤ በሰማይም ገሃነመ እሳት ይጠብቀናል፡፡ ይህን እውነት በመረዳት ዂላችንም በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተን ልንኖር ያስፈልጋል፡፡ ‹‹… ምሣር በዛፎች ሥር ተቀምጧል፤ እንግዲህ መልካም ፍሬ የማያደርግ ዛፍ ዂሉ ይቈረጣል፤ ወደ እሳትም ይጣላል›› (ማቴ. ፫፥፲) ተብሎ እንደ ተጻፈው ፍሬ የማያፈሩ ዕፀዋት በምሣር ተቈርጠው እንዲጣሉ እኛም ያለ መልካም ሥራ ከኖርን በእግዚአብሔር ዘለዓለማዊ ፍርድ ከገነት፣ ከመንግሥተ ሰማያት እንባረራለን፡፡ ይህ ክፉ ዕጣ እንዳይደርስብን ከሃይማኖታችን ሥርዓት፣ ከቤተ ክርስቲያናችን ትምህርት ሳንወጣ የቅዱሳንን ሕይወት አብነት አድርገን ለጽድቅ ሥራ እንሽቀዳደም፡፡ ‹‹እንግዲህ እነዚህን የሚያኽሉ ምስክሮች እንደ ደመና በዙሪያችን ካሉልን እኛ ደግሞ ሸክምን ዅሉ ቶሎም የሚከበንን ኀጢአት አስወግደን የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን ተመልክተን በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ፤›› በማለት ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረን (ዕብ. ፲፪፥፩-፪)፡፡

ይቆየን

ክረምት – ካለፈው የቀጠለ

በመጋቤ ሐዲስ ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

ነሐሴ ፳፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የተዘራው ዘር በዝናቡና በተዘራበት አፈር አማካይነት ይፈርሳል፤ ይበቅላል፤ ይለመልማል፤ ያብባል፤ ፍሬ ይሰጣል፡፡ ሰውም እንደዚሁ ነው፡፡ ይፀነሳል፤ ይወለዳል፤ ያድጋል፤ ይሞታል፡፡ ወደ መሬት ይመለሳል፤ ይፈርሳል፡፡ ትንሣኤ ዘጉባኤን ጠብቆ ይነሣል፡፡ ይህን በተመለከተ ‹‹የስንዴ ቅንጣት በምድር ወድቃ ካልሞተች ብቻዋን ትቀራለች፡፡ ብትሞት ግን ብዙ ፍሬ ታፈራለች፤›› በማለት ጌታችን አስተምሯል (ዮሐ. ፲፪፥፳፬)፡፡ ሰውም ካልሞተ አይነሣም፤ ካልተነሣም መንግሥተ ሰማያት ሊገባ አይችልምና፡፡ ምክንያቱም ግብር እምግብር ሳይለወጡ መንግሥተ ሰማያት መግባት አይቻልምና፡፡ ስለዚህ ሰው ትንሣኤ እንዳለው ገበሬ ከሚዘራው ዘር መማርና ብዙ ፍሬ ማፍራት ይጠበቅበታል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ትንሣኤ ሙታንን ባስተማረበት መልእክቱ ወርኃ ዘር የትንሣኤ ሙታን መማሪያ መኾኑን አስረድቷል፡፡ ሐዋርያው ‹‹ነገር ግን ሰው ሙታን እንዴት ይነሣሉ? በምንስ አይነት አካል ይመጣሉ? የሚል ይኖር ይኾናል፡፡ አንተ ሞኝ፣ የቆሮንቶስ ገበሬ አንተ የዘራኸው ካልሞተ ሕያው አይኾንም፡፡ የምትዘራውም ስንዴ ቢኾን ከሌላም ዓይነት (በቆሎ፣ ኑግ) የአንዱ ቢኾን ቅንጣት (ፍሬ) ብቻ ነው እንጂ የምትዘራው የሚኾነውን አካል አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ግን እንደ ወደደ አካልን ይሰጠዋል፤›› በማለት አስተምሯል (፩ኛ ቆሮ. ፲፭፥፴፭)፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ተናገረው የሰው ልጅ እንደ ዘር በመበስበስ ይዘራል፤ በአለመበስበስ ይነሣል፡፡ በውርደት (አራት አምስት ሰው ተሸክሞት) ይዘራል፤ ይቀበራል፤ በክብር ይነሣል፡፡ በድካም ይዘራል፤ በኀይል ይነሣል፡፡ በፍጥረታዊ አካል ይዘራል፤ ሟች፣ ፈራሽ፣ በስባሽ አካል ይቀበራል፡፡ በመንፈሳዊ አካል ይነሣል ማለት የማይሞት፣ የማይታመም፣ የማይደክም ኾኖ ይነሣል ማለት ነው፡፡ ከዚህ ላይ አንድ ገበሬ ስንዴ ከዘራ ስንዴ፣ ጤፍ ከዘራ ደግሞ ጤፍ፣ በቆሎም ከዘራ በቆሎ፣ ኑግ ቢዘራ ኑግ እንደሚኾን አካሉን ለውጦ እንደማይበቅል ሰውም የራሱን ማንነት ይዞ የሚነሣ መኾኑንም ጭምር ነው ያስተማረን፡፡ ሰው ክፉ የሠራም፣ ጽድቅ የሠራም የራሱን ሥራ ይዞ ይነሣል እንጂ ጻድቁ ኀጥእ ኀጥኡ ጻድቅ ኾኖ አይነሣም፡፡ እንደ ሥራው ዋጋውን የሚቀበልበት ነውና፡፡ ‹‹ሰው የዘራውን ያጭዳል›› እንዲል (ገላ. ፮፥፯)፡፡ በሌላ አንቀጽ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፤ ‹‹በጥቂት የሚዘራ በጥቂት ያጭዳል፤ በበረከትም የሚዘራ ደግሞ በበረከት ያጭዳል፤›› (፪ኛ ቆሮ. ፱፥፮)፡፡ ይህንም ስለ መስጠትና መቀበል አስተምሮታል፡፡ የዘራ እንደሚሰበስብ፣ የሰጠም ዋጋውን አያጣምና የተዘራባት ምድር የዘሩባት አብዝታ እንደምትሰጥ፣ በምጽዋት መልክ የተቀበሉ ነዳነያንም ትልቅ ዋጋ ያሰጣሉና በሚያልፍ የማያልፍ፤ በሚያልቅ የማያልቅ ዋጋ ያስገኛሉና፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ምጽዋትን በዘር መስሎታል፡፡ ‹‹ዘርን ለዘሪ፣ ለመብላትም እንጀራን በብዙ የሚሰጥ እርሱም የምትዘሩትን ዘር ይሰጣችኋል፤›› እንዲል (፪ኛ ቆሮ. ፱፥፲)፡፡

‹‹ብዙ ጊዜ በእርሷ ላይ የሚወርደውን ዝናም የምትጠጣ መሬት ለሚያርሷትም ደግሞ የምትጠቅምን አትክልት የምታበቅል ከእግዚአብሔር በረከትን ታገኛለችና፡፡ እሾኽንና ኩርንችትን ግን ብታወጣ የተጣለች ናት፡፡ ለመርገምም ትቀርባለች መጨረሻዋ መቃጠል ነው፤›› (ዕብ. ፮፥፯) ተብሎ እንደ ተጻፈ መሬት የተባለ የሰው ልጅ፤ ዘር የተባለ ደግሞ ቃለ እግዚአብሔር ነው፡፡ ዝናም የተባለ ትምህርት፤ እሾኽ የተባለ ኀጢአት፣ ክፋት ነው፡፡ ምድር የዘሩባትን ባታበቅል መጨረሻዋ መቃጠል እንደ ኾነ ዅሉ የሰው ልጅም አደራውን ባይጠብቅ፣ የንስሐ ፍሬ ባያፈራ ፍጻሜው መከራ ይኾናል፡፡ ሰው እንደ ዘር ወደ መሬት እንደሚመለስ ዘሩ ፈርሶ፣ በስብሶ ከበቀለ በኋላ ፍሬ እንደሚሰጥ ሰውም ከሞተ በኋላ ትንሣኤ ያለው መኾኑን በማሰብ መልካም ሥራን መሥራት ይገባናል፡፡ ከዚህ አለፍ ብለን ዘር የሚለውን ቃል ስንመለከተው ድንቅ ምሥጢር ያዘለ መኾኑን እንገነዘባለን፡፡ ‹‹የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ዘርን ባያስቀርልን ኖሮ እንደ ሰዶም በኾንን፤ ገሞራንም በመሰልን ነበር፤›› እንዳለ (ኢሳ. ፩፥፱)፡፡ ይህም እኛን ለማዳን ከእናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደውን ክርስቶስን ያመላክታል፡፡ ‹‹የነሣውን ሥጋ ከመላእክት የነሣው አይደለም፡፡ ከአብርሃም ዘር ነው እንጂ፤›› እንዲል (ዕብ. ፪፥፲፮)፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ይህ ዘር ምን ያህል ታላቅ መኾኑን ሲያስረዳ ‹‹ዳግመኛ የተወለዳችሁት ከሚጠፋ ዘር አይደለም፤ በሕያውና ለዘለዓለም በእግዚአብሔር ቃል ከማይጠፋ ዘር ነው እንጂ፤›› (፩ኛ ጴጥ. ፩፥፳፫)፡፡ የማይጠፋ ዘር የተባለውም ክርስቶስ ነው፡፡ ከእርሱ ተወልደናልና እርሱንም በመከራው መስለነው በትንሣኤውም ልንመስለው ያስፈልጋል፡፡

፫. ክረምት ወርኃ ልምላሜ ነው

በክረምት ወቅት ከዘር ተከትሎ ምድር በቅጠል በልዩ ልዩ የልምላሜ ዓይነቶች አሸብርቃ፣ ደምቃ በዋዕየ ፀሐይ የተራቆተ ማንነቷ በቅጠል የሚሸፈንበት ወቅት ነው፡፡ በመኾኑም ወቅ ወርኃ ልምላሜ ነው፡፡ ፍሬ ግን የለም፤ ይህን ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ ‹‹ሰማይን በደመና ይሸፍናል፤ ለምድርም ዝናምን ያዘጋጃል፡፡ ሣርን በተራሮች ላይ ያበቅላል፤ ለምለሙንም ለሰው ልጆች ጥቅም፡፡ ለሚጠሩት ለቍራ ጫጩቶች ለእንስሶችም ምግባቸውን ይሰጣል፤›› (መዝ. ፻፵፮፥፰-፲) በማለት ወቅቱ የልምላሜ፣ የሣርና የቅጠል፤ እንስሳት ሣር ቅጠሉን ከማንኛውም ጊዜ በበለጠ የሚያገኙበት ወቅት እንደ ኾነ ገልጿል፡፡ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው በቢታንያ መንገድ ላይ በተራበ ጊዜ ያያት በለስ ቅጠል ብቻ እንደ ነበረች፤ ጌታችንም ‹‹ለዘለዓለሙ ፍሬ አይገኝብሽ›› ብሎ እንደ ረገማት፤ በለሲቱም ወዲያውኑ እንደ ደረቀች በወንጌል ተጽፏል (ማቴ. ፳፩፥፲፰)፡፡ ያ ጊዜ የክረምት ወቅት (የቅጠል ወቅት) ነበር፡፡ ይህም በነቢያት ዘመን ይመሰላል፡፡ በዘመነ ነቢያት ዅሉም በተስፋ ብቻ ይኖሩ ነበር፡፡ ‹‹ብዙ ነቢያትና ጻድቃን ሊያዩ ተመኙ፤ አላዩም፡፡ የምትሰሙትን ሊሰሙ ተመኝተው አልሰሙም፤›› እንዳለ ጌታችን (ማቴ. ፲፫፥፲፮)፡፡ ገበሬውም የዘራውን ዘር መብቀል በተስፋ እየተመለከተ፣ አረሙን እየነቀለ፣ ዙሪያውን እያጠረ፣ እየተንከባከበ ይጠብቃል፡፡ ደግሞም ፈጣሪውን ከበረድ እንዲጠብቅለት እየተማጸነ የራት ሰዓት እስኪደርስ መቆያ እንዲቀምስ ይህ ቅጠል ፍሬ እስኪሰጥም በተስፋ አለኝ እያለ ቅጠሉን የዐይን ምግብ አድርጎ ይጠባበቃል፡፡

በሌላ መልኩ የእግዚአብሔር መንግሥት ዘሪ በእርሻው ላይ የዘራውን ዘር እንደምትመስል ተጽፏል፡፡ ‹‹በምድር ዘርን እንደሚዘራ ሰው የእግዚአብሔር መንግሥት እንዲህ ናት፡፡ ሌሊት ይተኛል፤ ቀን ይነሣል፡፡ እርሱም (ገበሬው) እንዴት እንደሚኾን ሳያውቅ ዘሩ ይበቅላል፤ ያድግማል፡፡ ምድሪቱም አውቃ በመጀመሪያ ቡቃያ፣ ኋላም ዛላ፣ በዘለላው ፍጹም ፍሬ ታፈራለች፡፡ ፍሬው ሲበስል መከር ደርሷልና ወዲያው ማጭድ ይልካል፤›› እንዳለ (ማር. ፬፥፳፮-፳፱)፡፡ በገበሬ የተመሰለው ኢየሱስ ክርስቶስም እኛ በዓለም ላይ ያለን የሰው ዘሮች በሙሉ በመከር ያፈራውም ያላፈራውም እንደሚሰበሰብ ያሳየናል፡፡ ‹‹እንግዲህ ወንድሞች ሆይ፣ ጌታ እስኪመጣ ድረስ እነሆ ገበሬው የፊተኛውን፣ የኋለኛውን ዝናም እርሱን የታገሠ የከበረውን የምድር ፍሬ ይጠብቃል፡፡ እናንተም ደግሞ ታገሡ፤›› እንዳለ ሐዋርያው (ያዕ. ፭፥፯-፱)፡፡ ገበሬ ቅጠሉ ፍሬ እስከሚሰጥ ምን ያህል መከራን እንደሚታገሥ እኛም መንግሥተ ሰማያት ለመግባት ቅጠል ብቻ የኾነ ማንነታችን የንስሐ ፍሬ እስኪያፈራ ድረስ መከራውን መታገሥ ይገባናል፡፡ ምድራዊ ፍሬ ለማግኘት ይህን ያህል መጠበቅና መታገሥ ካስፈለገ ሰማያዊ ዋጋ ለመቀበል ምን ያህል መታገሥ ያስፈልግ ይኾን? ከወርኃ ቅጠል ያለ ፍሬ ብንገኝ መርገምን እንደምናተርፍ፣ ብናፈራ ግን ገበሬ ምርቱን ደስ ብሎት እንዲሰበስብ ፈጣሪያችንም በእኛ እንደሚደሰትና ዋጋችንን እንደሚሰጠን እንማራለን፡፡ ክረምት ጥልቅ ትምህርት የምንማርበት እግዚአብሔር በሰፊው የሚገለጽበት ወቅት ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ክረምት – የመጀመርያ ክፍል

በመጋቤ ሐዲስ ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

ነሐሴ ፳፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹ክረምተ ወሐጋየ ዘአንተ ፈጠርከ፤ በጋንም ክረምትንም አንተ አደረግህ፤›› (መዝ. ፸፫፥፲፯) በማለት ቅዱስ ዳዊት እንደ ገለጸው እግዚአብሔር አምላክ የዓለምን ምግብ ሥጋዊውንም መንፈሳዊውንም በአራት ወቅት ከፍሎታል፡፡ ሥጋዊውን በአራቱ ክፍላተ ዘመን፤ መንፈሳዊውን በአራቱ ወንጌላዊያን ትምህርት፡፡ የሰው ልጅ ሥጋዊ ምግብና ከአራቱ ክፍላተ ዘመን እንደማይወጣ ዅሉ መንፈሳዊ ምግብናውም ከአራቱ ወንጌላውያን አይወጣም፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር የሥጋም የነፍስም ፈጣሪ፣ መጋቢ ነውና፡፡ ከአራቱ ክፍላተ ዘመን አንዱ አሁን የምንገኝበት ዘመነ ክረምት ነው፡፡ በዘመነ ክረምት ከሥጋዊ ምግብ ያለፈ መንፈሳዊ ምግብም እናገኛለን፡፡

ክረምት ምንድን ነው?

ክረምት ማለት ‹ከርመ – ከረመ› ካለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲኾን ‹መክረም፣ የዓመት መፈጸም፣ ማለቅ፣ መጠናቀቅ› ማለት ነው፡፡ ክረምት፣ በፀሐይ የደረቁ ኮረብቶች፣ ተራሮች በዝናም አማካይነት ውኃ የሚያገኙበትና በልምላሜ የሚሸፈኑበት፤ የደረቁ ወንዞች፣ ጉድጓዶች በውኃ የሚሞሉበት፤ በፀሐይ የተቃጠለች ምድር ከሰማይ በሚወርድ ጠል በረከት የምትረካበት፤ በውኃ ጥም የተሰነጣጠቁ የምድር ጉረሮዎች ውኃን የሚጠግቡበት፤ ሰማይ በደመና፣ የተራሮች ራስ በጉም የሚሸፈኑበት፤ በሙቀት ፋንታ ቅዝቃዜ፣ በድርቅ ፈንታ ልምላሜ የሚነግሥበት፤ ተሰባብሮ የወደቀ ሐረግ (ተክል) ቀና ብሎ የሚቆምበት፣ የሚያድግበት ወቅት ነው፡፡

፩. ክረምት ወርኃ ማይ (የውኃ ወቅት) ነው

ውኃ፣ እግዚአብሔር አምላክ ለፈጠረው ፍጥረት ዅሉ በጣም አስፈላጊ ፍጥረት ነው፡፡ ምድር የዘሩባትን እንድታበቅል፣ የተከሉባትን እንድታጸድቅ፣ ያጸደቀችውን ተክልም ለፍሬ እንድታበቃ ውኃ አስፈላጊ ነው፡፡ ያለ ውኃ ለምግብነት የሚውል ነገር በዓለማችን ውስጥ የለም፡፡ ምግብ የሚዘጋጀውም የሚወራረደውም በውኃ ነው፡፡ ‹‹ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡ? ውኃ ቢያንቅ በምን ይውጡ?›› በማለት አበው የውኃን ጥቅም ያስረዳሉ፡፡ ቁሳቁሱ የሚታጠበው፤ ቤት የሚሠራው፤ ሕንጻ የሚገነባው በውኃ ነው፡፡ በባሕርም በየብስም ለሚኖሩ፤ ለምግብነት ለሚዉሉትም ለማይዉሉትም ውኃ አስፈላጊ ነው፡፡ እንስሳትም፣ እፀዋትም፣ ምድርም ውኃ ይፈልጋሉ፡፡ በጠቅላላው የፍጡራን ሕይወት የውኃ ጥገኛ ነው፡፡ የሰው ልጅ የሚጠቀምባቸው ፍጡራን ዅሉ ያለ ውኃ ምግብ አይሰጡም፡፡ ስለዚህ ከፍጡራን በተለየ መልኩ ውኃ ለሰው ልጅ ያስፈልገዋል፡፡ በዓለማችን ብዙውን ቦታ የሚሸፍነው ውኃ መኾኑን ሥነ ፍጥረትም ሳይንስም ይስማሙበታል፡፡ ምክንያቱም በምድር ላይ ካለ ፍጡር ውኃ የማያስፈልገው የለምና፡፡

ከዚህ አለፍ ብለን ስንመለከት በአርአያ ሥላሴ የተፈጠረ የሰው ልጅ ከተፈጠረባቸው አራት ባሕርያት አንዱ ውኃ ነው፡፡ የሰው ልጅ በመሬትነት ባሕርዩ እየፈረሰና እየተቆረሰ ዓለምን እንዳያጠፋ በውኃነት ባሕርዩ አንድነቱ ጸንቶለት ይኖራል፡፡ በእሳትነት ባሕርዩ ዓለምን እንዳያቃጥል በውኃነት ባሕርዩ እየቀዘቀዘ ይኖራል፡፡ ሰው ከእናቱ ተወልዶ የእናቱን ጡት ጠብቶ እንዲያድግ ሰውም ከውኃ፣ ከእሳት፣ ከነፋስና ከመሬት ተፈጥሮ እነዚሁ የተገኘባቸውን እየተመገበ በምድር ይኖራል፡፡ የአራቱ ባሕርያት አስታራቂ ሽማግሌ ውኃ ነው፡፡ ጠበኞች የኾኑ ነፋስና መሬት በውኃ ይታረቃሉ፡፡ ነፋስ መሬትን ይጠርገዋል፡፡ መሬትም ነፋስን ይገድበዋል፡፡ ዝናም በዘነመ ጊዜ ትቢያው (የመሬት ላይኛው ክፍል) በውኃ አማካይነት ከታችኛው ክፍል ጋር አንድ ይኾናል፤ በነፋስ ከመወሰድም ይተርፋል፡፡

ከዚህም ሌላ ውኃ የእግዚአብሔር መሣሪያ ነው፡፡ የሰው ልጆች ሕገ እግዚአብሔርን ሲጥሱ፣ ትእዛዘ እግዚአብሔርን ሲያፈርሱ ከሥርዓቱ ሲወጡ፣ ከአምልኮቱ ሲያፈነግጡ ውኃ መቅጫ መሣሪያ ነው፡፡ ለምሳሌ በኀጢአት የተበላሸው፣ የቆሸሸው ዓለም የተቀጣው በውኃ ነው (ዘፍ. ፮፥፩፤ ፯፥፩፤ ፰፥፩)፡፡ ነቢዩ ኤልያስ፣ አምልኮተ እግዚአብሔርን በአምልኮተ ጣዖት ተክተው፣ ሃይማኖተ ኦሪትን ትተው፣ የጣዖት ውሽማ አበጅተው ያስቸገሩትን አክአብና ኤልዛቤልን እንደዚሁም መሰሎቻቸውን የቀጣው ዝናም ለዘር፣ ጠል ለመከር እንዳይሰጥ ሰማይን ለጉሞ፣ ዝናምን አቁሞ ነው፡፡ በአንጻሩ በረድና እሳት አዝንሞ እንደ ነበርም መጽሐፍ ቅዱስ ያስረዳናል፡፡ ‹‹ኤልያስ እንደኛ የኾነ ሰው ነበር፡፡ ዝናም እንዳይዘንም አጥብቆ ጸለየ፤ በምድርም ላይ ሦስት ዓመት ከስድስት ወር ዝናም አልዘነበም፡፡ ሁለተኛም ጸለየ፤ ሰማዩም ዝናብን ሰጠ፤ ምድር ፍሬዋን አበቀለች፤›› በማለት ሐዋርያው እንደ ተናገረው (ያዕ. ፭፥፲፯)፡፡

ውኃ እስከ አሁን የተመለከትነው በሥጋዊ ምግብነቱ የሚሰጠውን አገልግሎት ነው፡፡ ውኃ መንፈሳዊ ምግብና (ምግብነት ወይም አገልግሎት) አለው፡፡ ደገኛዋ የሰው ልጆች ጥምቀት በውኃ መፈጸሟ የውኃ ጥቅም የጎላ መኾኑን ያሳየናል፡፡ የጥምቀታችን መሥራች ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአባቶቻችንና በእኛ ላይ የነበረውን የዕዳ ደብዳቤ ያጠፋልን በውኃ ተጠምቆ ነውና (ማቴ. ፫፥፲፫)፡፡ ‹‹ከውኃና ከመንፈስ ያልተወለደ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ዮሐ. ፫፥፭)፡፡ ይኸውም ውኃ ከሥጋዊ ምግብናው ባሻገር እኛ የእግዚአብሔር ልጆች የምንኾንበት ምሥጢር መፈጸሚያ መኾኑን ያስረዳል፡፡ በሌላ መልኩ ጌታችን የእኛን ሥጋ ለብሶ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተገልጾ ባስተማረ ጊዜ ‹‹እንጀራ ለመነ›› ሳይኾን ‹‹ውኃ ለመነ›› ተብሎ ነው የተነገረለት፡፡ ‹‹ውኃ አጠጪኝ አላት›› እንዲል (ዮሐ. ፬፥፯)፡፡ እስራኤልን ዐርባ ዓመት ውኃ ከጭንጫ እያፈለቀ ያጠጣ አምላክ ውኃ የለመነው ውኃ አጥቶ አይደለም፡፡ ውኃ ትልቅ ምሥጢር የሚፈጸምበት መኾኑን ለመግለጽ ነው እንጂ፡፡ ይኸውም ሊታወቅ ‹‹የእግዚአብሔርን ስጦታና ውኃ አጠጪኝ የሚልሽ ማን መኾኑን ብታውቂስ አንቺ ደግሞ በለመንሺው፤ እርሱም የሕይወትን ውኃ በሰጠሸ ነበር … እኔ ከምሰጠው ውኃ የሚጠጣ ለዘለዓለም አይጠማም፤›› በማለት አስተምሮአል፡፡

ጌታችን በመስቀል ላይ ከተናገራቸው ሰባቱ ንግግሮች አንዱ ‹‹ተጠማሁ›› የሚል ነበር (ዮሐ. ፲፱፥፳፱)፡፡ ይህ ከሥጋ መጠማት ያለፈ የእኛን የነፍሳችን ጥማት እንደ አጠፋልን የምንማርበት ነው፡፡ እኛን የሕይወት ውኃ ያጠጣን ዘንድ ተጠማሁ አለም፤ በዓለም ላሉ ፍጡራን ዅሉ ውኃ አስፈላጊ ቢኾንም ቅሉ በተለይ ለሰው ልጆች እጅግ አስፈላጊ እንደ ኾነ ሲያስረዳም ነቢዩ ኢሳይያስ እንዲህ ሲል ተናገረ፤ ‹‹እናንተ የተጠማችሁ ዅሉ ወደ ውኃ ኑ፤ ገንዘብም የሌላችሁ ኑና ግዙ፤›› (ኢሳ. ፶፭፥፩)፡፡ ‹‹የተጠማ ይምጣ፤ ይጠጣ፤›› የሚለው ኃይለ ቃል ብዙ ምሥጢር አለው፡፡ ጌታችን የአይሁድ በዓል በሚከበርበት ቦታ ተገኝቶ ቀደም ሲል በኢሳይያስ የተነገረው ቃል ስለ መንፈስ ቅዱስ የተነገረ መኾኑን ገልጿል፡፡ ‹‹ኢየሱስም ቆሞ ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ፡፡ በእኔ የሚያምን መጽሐፍ እንዳለ የሕይወት ውኃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል ብሎ ጮኸ፡፡ ይኼን ግን በእርሱ የሚያምኑ ሊቀበሉት ስለ አላቸው ስለ መንፈስ ቅዱስ ተናገረ፤›› እንዲል (ዮሐ. ፯፥፴፯-፴፱)፡፡ ስለዚህ ውኃ የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌ ኾኗል ውኃ ከቆሻሻ፣ ከዕድፍ እንዲያነጻ መንፈስ ቅዱስም ከኀጢአት፣ ከርኵሰት፣ ከክፋት፣ ከተንኮል፣ ከበደል ሰውን ያነጻልና፡፡

፪. ክረምት ወርኃ ዘር (የዘር ወቅት) ነው

ገበሬው በበጋ ያረሰውን የከሰከሰውን ደረቅ መሬት በዝናብ ወቅት አለስልሶ አዘጋጅቶ ከጎታው ወይም ከጎተራው ያስቀመጠውን ዘር ባዘጋጀው መሬት ላይ አውጥቶ ይዘራል፡፡ መሬቱ ያብቅል አያብቅል ፍሬ ይስጥ አይስጥ ሳያውቅ እግዚአብሔር በዝናብ አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ ይመግበኛል ብሎ በማመን ያለ ምንም ጥርጥር የጎታውን እኽል ለመሬት አደራ ይሰጣል፡፡ ከላይ ዝናሙን ከታች ጭቃውን ታግሦ በሬዎችን እየነዳ በትከሻው ላይ ዘርና ቀምበር ተሸክሞ ዘር ለመዝራት ይሰማራል፡፡ የገበሬውን ኹኔታ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲህ ብሎ ገልጾታል፤ ‹‹ዘሪ ሊዘራ ወጣ፤ ሲዘራም አንዳንዱ ዘር ከመንገድ ዳር ወደቀ፡፡ በጭንጫ ላይ የወደቀ ዘር አለ፡፡ በእሾኽ መካከል የወደቀ ዘርም አለ፡፡ በመልካም መሬት ላይም የወደቀ ዘር አለ፡፡ መቶ፣ ስልሳ፣ ሠላሳ ፍሬ ሰጠ፤›› (ማቴ. ፲፫፥፩)፡፡ ጌታችን ራሱን በገበሬ፣ ቃሉን በዘር፣ የሰማዕያንን ልቡና በመንገድ፣ በዐለት፣ በእሾኽ፣ በለሰለሰ መሬት መስሎ አስተምሯል፡፡ በመንገድ የተመሰለው ሰምተው የማያስተውሉ ሰዎች ልቡና ነው፡፡ የሰማይ ወፎች የተባሉ ደግሞ አጋንንት ናቸው፡፡ ‹‹ኢትሕሚ ሰብአ በቤትከ እስመ ዖፈ ሰማይ ያወጽዖ ለነገርከ፤ የሰማይ ወፍ (ሰይጣን) ቃልህን ያወጣዋልና፣ ክንፍ ያለውም ነገርህን ያወራዋልና በልብህ ዐሳብ እንኳን ቢኾን ንጉሥን አትሳደብ፤ በመኝታ ቤትህም ባለ ጠጋን አትማ፤›› እንዳለ ጠቢቡ ሰሎሞን (መክ. ፲፥፳)፡፡

በዐለት የተመሰሉት ፈጥነው የሚሰሙ ግን ተግባር ላይ የሌሉ በእሾኽ የተመሰሉትም የዚህ ዓለም ዐሳብ፣ ምድራዊ ብልጽግና፣ ፍቅረ ዓለም አስሮ የያዛቸው ሰዎች ናቸው፡፡ በመልካም መሬት የተመሰሉት ደግሞ ቃሉን ሰምተው የጽድቅ ሥራን የሚሠሩ ናቸው፡፡ በወርኃ ዘር የምንማረው ትልቁ ትምህርት ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን ነው፡፡ በወርኃ ማይ ምሥጢረ ጥምቀትን እንደተማርን ገበሬው በጎታው ያከማቸውን እኽል ከአፈር ጋር አንድ እንደሚያደርገው ማለት በአፈር ላይ እንደሚዘራው የሰው ዘርም እንዲሁ ‹‹ውሎ ውሎ ከቤት ኖሮ ኖሮ ከመሬት›› እንዲሉ ሲሞት በመቃብር ከአፈር ጋር አንድ ይኾናል፤ ይፈርሳል ይበሰብሳል፤ ወደ አፈርነቱ ይመለሳል፡፡ ‹‹ወደ ወጣህበት መሬት እስክትመለስ ድረስ በፊትህ ወዝ እንጀራን ትበላለህ፡፡ አፈር ነህና ወደ አፈርነትህም ትመለሳለህና፤›› እንዳለ (ዘፍ. ፫፥፲፱)፡፡

ይቆየን

ዘመነ ክረምት – ክፍል ስድስት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ተከታታዮች! በክፍል አምስት ዝግጅታችን ሦስተኛውን የዘመነ ክረምት ንዑስ ክፍል በተለይ ደሰያትን እና ዓይነ ኵሉን መነሻ በማድረግ ወቅቱን የሚመለከት ትምህርት አቅርበን ነበር፡፡ በዚህ ዝግጅት ደግሞ አራተኛውን የዘመነ ክረምት ንዑስ ክፍል የሚመለከት ትምህርት ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡ መልካም ንባብ!

፬. ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን፣ መዓልት

ከነሐሴ ፳፰ እስከ ጳጕሜን ፭ (፮) ቀን (ከአብርሃም እስከ ዮሐንስ ዋይዜማ) ድረስ ያለው አራተኛው ክፍለ ክረምት ‹ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን መዓልት› ይባላል፡፡ በዚህ ክፍለ ክረምት ውስጥ በሚገኙ ቀናት እነዚህን ፍጥረታት የሚመለከቱ የቅዱሳት መጻሕፍት ክፍሎች በቤተ ክርስቲያናችን ይነገራሉ፤ ይተረጐማሉ፤ ይመሠጠራሉ፡፡ ‹ጎሕ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን፣ መዓልት› ዅሉም የግእዝ ቃላት ሲኾኑ ተመሳሳይ ትርጕምና ጠባይዕ ያላቸው ፍጥረታት ናቸው፡፡ ‹ጎህ፣ ነግህ እና ጽባሕ› – ንጋትን፣ ማለዳን፣ ሌሊቱ ወደ ቀን፤ ጨለማው ወደ ብርሃን የሚሸጋገርበትን ክፍለ ጊዜ ይገልጻሉ፡፡ ብርሃን ደግሞ የጨለማ ተቃራኒ፣ የፀሐይ ብርሃን የማይታይበት ክፍለ ዕለት ሲኾን ‹መዓልት› ማለትም በአንድ በኩል የፀሐይ ብርሃን የሚታይበት ጊዜን፣ በሌላ በኩል ደግሞ ከእሑድ እስከ ሰኞ ያሉትን፣ እንደዚሁም ከ፩ – ፴ የሚገኙ ዕለታትን ያመላክታል (ዘፍ. ፩፥፭-፴፩)፡፡

ስለ ንጋትና ብርሃን ለመናገር በመጀመሪያ ስለ ፀሐይ፣ ስለ ጨረቃ እና ከዋክብት አፈጣጠር በጥቂቱ ማስታወስ ያስፈልጋል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ በዕለተ ረቡዕ በመጀመሪያው ሰዓተ ሌሊት ‹‹ለይኩን ብርሃን፤ ብርሃን ይኹን›› ባለ ጊዜ ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብት ተፈጥረዋል፡፡ ‹‹እግዚአብሔርም ‹ብርሃን ይኹን› አለ፤ ብርሃንም ኾነ፡፡ እግዚአብሔርም ብርሃኑ መልካም እንደ ኾነ አየ፤ እግዚአብሔርም በብርሃኑና በጨለማው መካከል ለየ፤ እግዚአብሔርም ብርሃኑን ‹ቀን›፣ ጨለማውንም ‹ሌሊት› ብሎ ጠራው፤›› እንዲል (ዘፍ. ፩፥፫-፬)፡፡ የፀሐይ ተፈጥሮዋ ከእሳትና ከነፋስ ሲኾን ጨረቃንና ከዋክብትን ደግሞ ከነፋስና ከውኃ አርግቶ ፈጥሯቸዋል፡፡ ሲፈጥራቸውም ከዅሉም ፀሐይን፤ ከከዋክብት ደግሞ ጨረቃን አስበልጦ ነው፡፡ የፈጠራቸውም እርሱ ሊጠቀምባቸው ሳይኾን ለሰው ልጅ እና በዚህ ዓለም ለሚገኙ ፍጥረታት እንዲያበሩ ነው፡፡ እነዚህ የብርሃን ምንጮች (ፀሐይ እና ጨረቃ) ልዩ ልዩ ምሳሌያት አሏቸው፤ ከእነዚህ መካከልም በጻድቃንና በኃጥኣን መመሰላቸው አንደኛው ነው፡፡

ጻድቃን ዅልጊዜ በምግባር፣ በሃይማኖት ምሉዓን በመኾናቸው በፀሐይ፤ ኃጥኣን ደግሞ በምግባር አንድ ጊዜ ሙሉ፣ ሌላ ጊዜ ጐደሎ ማለትም አንድ ጊዜ ደግ ሌላ ጊዜ ክፉ እየኾኑ ግብራቸውን በመለዋወጥ ይኖራሉና በጨረቃ ይመሰላሉ፡፡ የፀሐይ እና ጨረቃ አካሔዳቸው በሰማይና በምድር መካከል ነው፡፡ ጻድቃንም በተፈጥሯቸው ምድራውያን ኾነው ሳሉ ሰማያዊውን መንግሥት ይወርሳሉ፡፡ ፀሐይ እና ጨረቃ ሠሌዳቸው ከነፋስ፣ ከእሳትና ከውኃ ነው፡፡ እነዚህ ሦስቱ ጠባይዓት እርስበርስ ተስማምተው ብርሃንን እንዲሰጡ አድርገዋቸዋል፡፡ ስለዚህም በነፋሱ ፍጥነት፣ በእሳቱ ሙቀት፣ በውኃው ቅዝቃዜ ይስማማቸዋል፡፡ ይህም የመምህራን መንፈሳዊ ቍጣ ምሳሌ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን መምህራን ጠባያቸው እንደ ውኃ የቀዘቀዘ ቢኾንም የእግዚአብሔርን ክብር የሚያቃልሉ፣ ቅዱሳንን የሚጥላሉ፣ የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ የሚፃረሩ መናፍቃን ሲመጡ ግን እንደ ነፋስ በሚፈጥን፣ እንደ እሳት በሚያቃጥል መንፈሳዊ ቍጣ ተነሣሥተው ይገሥፃሉ፤ ይመክራሉ፤ ያስተምራሉ፡፡ አንድም እነዚህ ሦስቱ የፀሐይ እና የጨረቃ ሠሌዳዎች የሥላሴ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ይኸውም እሳት በመለኮት፤ ውኃ በትስብእት፤ ነፋስ በመንፈስ ቅዱስ ይመሰላል (መጽሐፈ ሥነ ፍጥረት፣ አንድምታ ትርጓሜ)፡፡

በሌላ ምሥጢር ስንመለከታቸው ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን፣ መዓልት ወይም ዅሉንም በአጠቃላይ በብርሃን ምንጭነት ወይም በብርሃን ብንሰይማቸው የብርሃን ምንጭ ወይም ብርሃን እግዚአብሔር ነው፡፡ እርሱ በጨለማው ዓለም፤ በጨለማው ሕይወታችን፤ በጨለማው ኑሯችን የሕይወትን ወጋገን፣ ንጋት፣ ብሩህ ቀን የሚያወጣ አምላክ ነውና (ዮሐ. ፩፥፭-፲)፡፡ ለዚህም ነው ‹‹እግዚአብሔር ብርሃኔና መድኀኒቴ ነው፤ የሚያስፈራኝ ማነው?›› በማለት ቅዱስ ዳዊት የሚዘምረው (መዝ. ፳፮፥፩)፡፡ ስለ ኾነም እኛ ክርስቲያኖች ብርሃን በተባለ በእግዚአብሔር መታመን ያስፈልገናል፡፡

ዳግመኛም የእግዚአብሔር ሕግ ብርሃን ይባላል፡፡ ብርሃን ጨለማን እንደሚያስወግድ ዅሉ የእግዚአብሔር ሕግም ከኀጢአት ባርነት፣ ከሲኦል እሳት ያድናልና፡፡ ‹‹ሕግህ ለእግሬ መብራት፤ ለመንገዴም ብርሃን ነው›› እንዳለ ቅዱስ ዳዊት (መዝ. ፻፲፰፥፻፭)፡፡ እንደዚሁም ብርሃን ክርስቲያናዊ ምግባርን ያመለክታል፡፡ ብርሃን ለራሱ በርቶ ለሌሎችም እንዲያበራ ክርስቲያናዊ ምግባርም ከራስ ተርፎ ለሰዎች ዅሉ ደምቆ በአርአያነት ይታያልና፡፡ እኛም ‹‹ብርሃን ሳለላችሁ በብርሃን ተመላለሱ›› ተብሎ እንደ ተጻፈ የጽድቅ ሥራ የማይገኝበት ጊዜ የጨለማ ዘመን ከመምጣቱ በፊት የጽድቅ ሥራ መሥራት በምንችልበት ጊዜ ዅሉ በመልካም ምግባር ጸንተን እንኑር (ዮሐ. ፲፪፥፴፭-፴፮፤ ፩ኛ ዮሐ. ፩፥፯)፡፡

ደግሞም መልካም ግብር ያላቸው ምእመናን በብርሃን ይመሰላሉ፤ ብርሃን በግልጽ ለሰዉ ዅሉ እንደሚታይና እንደሚያበራ መልካም ምግባር ያላቸው ምእመናንም በጽድቅ ሥራቸው ለብዙዎች አርአያ፣ ምሳሌ ይኾናሉና፡፡ ‹‹እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ፡፡ በተራራ ላይ ያለች ከተማ ልትሠወር አይቻላትም›› እንዳለ ጌታችን በወንጌል (ማቴ. ፭፥፲፬)፡፡ እንግዲህ ዅላችንም በጨለማ ከሚመሰለው ኀጢአት ወጥተን በብርሃን ወደሚመሰለው የጽድቅ ሕይወት ተመልሰን በክርስቲያናዊ ምግባር በርተን እኛ በርተን ወይም ጸድቀን ለሌሎችም ብርሃን ማለትም የጽድቅ ምክንያት ልንኾን ይገባናል፡፡ ‹‹ብርሃናችሁ በሰዉ ዅሉ ፊት ይብራ›› ተብለን ታዝዘናልና (ማቴ. ፭፥፲፮)፡፡

በአጠቃላይ ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን፣ መዓልት የሚባለው ክፍለ ክረምት ‹‹ቡሄ ካለፈ የለም ክረምት፤ ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት›› እንደሚባለው ክረምቱ እየቀለለ፣ ማዕበሉ እየቀነሰ፣ ዝናሙ እያባራ፣ ሰማዩ እየጠራ የሚሔድበት የንጋት፣ የወጋገን፣ የብርሃን ጊዜ ነው፡፡ ልክ እንደ ዘመኑ እኛም እንደ ደመና በልባችን የቋጠርነውን ቂምና በቀል፤ እንደ ጨለማ በአእምሯችን የሣልነውን ክፋትና ኑፋቄ ወይም ክህደት፤ እንደ ዝናምና ማዕበል በወገን ላይ ያደረስነውን ጥፋትና በደል በንስሐ ፀሐይ አስወግደን ወደ ብርሃኑ ሕገ እግዚአብሔር፤ ወደ ብርሃኑ ኢየሱስ ክርስቶስ፤ ወደ ብርሃኑ ምግባረ ሠናይ፤ ወደ ብርሃኑ ክርስትና እንመለስ፡፡ እንዲህ እንድናደርግም ልዑል እግዚአብሔር ‹‹በሕይወታችሁ ውስጥ ብርሃን ይኹን!›› ይበለን፡፡ እርሱ ‹‹ብርሃን ይኹን›› ካለ የኀጢአት ጨለማ በእኛ ላይ ለመሠልጠን የሚችልበት ዓቅም አያገኝምና፡፡

ይቆየን

እግዚአብሔር በደብረ ታቦር

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፲፬ ቀን ፳፻፱ .

‹እግዚአብሔር› የሚለው ቃል ሦስቱም አካላት (አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ) በጋራ የሚጠሩበት መለኮታዊ ስያሜ ነው፡፡ ‹‹አንሰ ሶበ እቤ እግዚአብሔር እብል በእንተ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ከመ በአሐዱ ስም ሥሉሰ ያምልኩ፤ እኔእግዚአብሔር› በአልኹ ጊዜ ስለ አብም፣ ስለ ወልድም፣ ስለ መንፈስ ቅዱስም እናገራለሁ፡፡ (ምእመናን) በአንዱ ስም (በእግዚአብሔር) ሦስቱ አካላትን ያመልኩ ዘንድ›› እንዳለ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ነባቤ መለኮት (ሃይማኖተ አበው)፡፡

ቅዱሳት መጻሕፍት እንደሚነግሩን እግዚአብሔር አምላካችን በብሉይም ኾነ በሐዲስ ኪዳን በአንድነቱም በሦስትነቱም በግብር (በሥራ)፣ በራእይ፣ በገቢረ ተአምራትና በልዩ ልዩ መንገድ ለፍጡራኑ ተገልጧል፡፡ በብሉይ ኪዳን በቅዱሳን ነቢያትና በመሳፍንት፣ በነገሥታት፣ በካህናትና በነቢያት ላይ በማደር፤ በጻድቃኑ ላይ ቸርነቱን፣ በክፉ አድራጊዎች ላይ ደግሞ መቅሠፍቱን በመላክ በልዩ ልዩ ምልክትና በተአምራት ይገለጥ ነበር፡፡ በሐዲስ ኪዳን ደግሞ ለአዳምና ለልጆቹ በገባው ቃል መሠረት የሰውን ሥጋ ለብሶ፣ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ በአካለ ሥጋ ተገልጦ በገቢረ ተአምራቱ፣ በትንሣኤውና በዕርገቱ አምላክነቱን አሳይቷል፡፡ የብሉይ ኪዳኑ መገለጥ በምልክት፣ በራእይ፣ በድምፅና በመሳሰሉት መንገዶች የተደረገ መገለጥ ነበር፤ የሐዲስ ኪዳኑ ግን አምላካችንን በዓይነ ሥጋ ያየንበት መገለጥ ስለ ኾነ ከዅሉም የተለየ ጥልቅ ምሥጢር አለው፡፡ ‹‹መቼም ቢኾን እግዚአብሔርን ያየው አንድ ስንኳ የለም፤ በአባቱ እቅፍ ያለ አንድ ልጁ እርሱ ተረከው›› (ዮሐ. ፩፥፲፰) በማለት ወንጌላዊው ዮሐንስ እንደ ገለጸው፡፡

እግዚአብሔር በሐዲስ ኪዳን ያደረዉን መገለጥ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ከምሥጢረ ሥላሴ ጋር በሚያያዙ ሦስት ዐበይት መንገዶች ይገልጹታል፡፡ ይኸውም በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ በዮርዳኖስና በደብረ ታቦር ላይ እንደ ኾነ ያስረዳሉ፡፡ ‹‹በላዕሌኪ ወበዮርዳኖስ ወበታቦር ሥልሰ ጊዜያተ ዘአልቦ ተውሳከ ወአልቦ ሕጸተ ለውሉደ ሰብእ ያርኢ ዘሥላሴሁ ገጻተ ጽጌኪ ድንግል ተአምሪሁ ከሠተ ወበፀዳሉ አብርሀ ጽልመተ›› እንዳለ ደራሲ (ማኅሌተ ጽጌ)፡፡ ትርጕሙም እግዚአብሔር አምላክ ጭማሬም ጉድለትም የሌለበት ሦስትነቱን ለሰው ልጅ ያሳይ ዘንድ በእመቤታችን፣ በዮርዳኖስ እና በታቦር ሦስት ጊዜ ተአምራቱንና ምሥጢረ መለኮቱን መግለጡን፤ በብርሃነ መለኮቱም ጨለማውን ዓለም ብርሃን ማድረጉን ያስረዳል፡፡ ይህም ጌታችን በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን ተወስኖ ሲወለድ፤ እንደዚሁም በዮርዳኖስ ወንዝ በተጠመቀበት ዕለት እግዚአብሔር አብ ‹‹የምወደው ልጄ እርሱ ነው፤ እርሱን ስሙት›› ብሎ  ሲመሰክር፣ መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል ወርዶ በራሱ ላይ ሲያርፍ፤ በተመሳሳይ መልኩ በደብረ ታቦር ብርሃነ መለኮቱን ሲገልጥ መለኮታዊ አንድነቱና አካላዊ ሦስትነቱ መታወቁን ያመለክታል፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን የምናቀርበው ትምህርትም እግዚአብሔር በደብረ ታቦር የመገለጡን ምሥጢር የተመለከተ ነው፡፡ መልካም ንባብ!

በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈው ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተስእሎተ ቂሣርያ በዋለ በስድስተኛው ቀን ማለትም ሐዋርያት ሰዎች ክርስቶስን ማን እንደሚሉት በተናገሩ፤ ቅዱስ ጴጥሮስም ክርስቶስ የባሕርይ አምላክ መኾኑን በመሰከረ በሳምንቱ (ነሐሴ ፲፫) ምሥጢረ መለኮቱን ይገልጥላቸው ዘንድ ጌታችን ሦስቱን ደቀ መዛሙርት መርጦ ወደ ረጅም ተራራ ይዟቸው ወጥቷል (ማቴ. ፲፯፥፩)፡፡ ይህ ተራራ ታቦር መኾኑንም ሐዋርያት በሲኖዶሳቸው ጠቅሰውታል፡፡ ሊቀ ነቢያት ሙሴ ከመቃብር ወጥቶ፤ ነቢዩ ኤልያስም ከብሔረ ሕያዋን መጥቶ በተገኙበት ጌታችን በተወለደ በ፴፪ ዓመት ከ፯ ወር ከ፲፭ ቀኑ፣ በዘመነ ማቴዎስ፣ ነሐሴ ፲፫ ቀን በዕለተ እሑድ በዚህ ተራራ ምሥጢረ መለኮቱን ገልጧል፡፡ (መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ በመ/ አፈወርቅ ተክሌ፣ አዲስ አበባ፣ ፳፻፭ ዓ.ም፤ ገጽ ፫፻፲፬፫፻፲፯ እና ፬፻፩)፡፡

የጌታችን ብርሃነ መለኮቱ ሲገለጥም ፊቱ እንደ ፀሐይ አበራ፤ ልብሱም ነጭ ኾነ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው፡፡ አንዱን ለአንተ፣ አንዱን፣ ለሙሴ አንዱን ለኤልያስ ሦስት ዳስ እንሥራ›› እያለ ተማጸነ፡፡ እንዲህ ማለቱም ጌታችን በተአምራቱ ሲራቡ እያበላቸው፣ ሲጠሙ እያጠጣቸው፣ ሲታመሙ እየፈወሳቸው፣ ቢሞቱ እያነሣቸው፤ ሙሴም እንደ ቀድሞው ደመና እየጋረደ፣ መና እያወረደ፣ ባሕር እየከፈለ፣ ጠላትን እየገደለ፤ ኤልያስ ደግሞ ሰማይን እየለጎመ፣ እሳት እያዘነመ፣ ዝናም እያቆመ አብረው በደብረ ታቦር እንዲኖሩ የነበረዉን መሻት ያመላክታል፡፡ የራሱን የሐዋርያትን ሳያነሣ የነቢያትን ስም መጥቀሱም በአንድ በኩል ትሕትናውንና ጌታችን አብሮ ያኖረኛል ብሎ ተስፋ ማድረጉን፤ በሌላ በኩል ደግሞ የክርስቶስን አምላክነት በሚገባ አለመረዳቱን ያመላክታል፡፡ ጌታችንን በተራራ ላይ በሰው ሠራሽ ቤት ይኖር ዘንድ ጠይቆታልና (ትርጓሜ ወንጌለ ማቴዎስ)፡፡

አምላከ ሰማይ ወምድር ክርስቶስ በሰው እጅ በተሠራ ቤት እንደማይኖር ይታወቅ ዘንድም ሰማያዊ ብሩህ ደመና ጋረደቻቸው፡፡ ‹‹በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት›› የሚል ቃል ከእግዚአብሔር አብ ዘንድ መጣ፡፡ ‹‹እርሱን ስሙት›› ማለቱም ጌታችን ዓለምን ለማዳን እንደሚሞት ሲናገር ቅዱስ ጴጥሮ ‹‹አይኹንብህ›› ብሎት ነበርና ‹‹እሞታለሁ›› ቢላችሁ ‹‹አትሞትም›› አትበሉት ሲል ነው፡፡ ሙሴና ኤልያስም ከጌታችን ጋር ሲነጋገሩ ተሰሙ፤ ስለ ክርስቶስ የተናገሩት ትንቢትም በደብረ ታቦር ተረጋገጠ፡፡ የፊቱን ግርማ ለማየትና የመለኮትን ድምፅ ለመስማት አልተቻላቸውምና ሙሴ ወደ መቃብሩ፣ ኤልያስም ወደ መጣበት ተመለሱ፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም የመለኮትን ፊት አይተው መቆም አልተቻላቸውምና ደንግጠው ወደቁ፡፡ ጌታችንም አጽናንቶ ኃይሉን ብርታቱን ካሳደረባቸው በኋላም እርሱ ከንቱ ውዳሴን የማይሻ አምላክ ነውና ዅሉም በጊዜው እስኪለጥ ድረስ ማለትም ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ተቀብለው የክርስቶስ አምላክነቱን፣ ሞቱን፣ ትንሣኤውን፣ ዕርገቱንና ዳግም ምጽአቱን ለዓለም እስኪሰብኩ ድረስ ያዩትም ምሥጢር ለማንም እንዳይነግሩ አዝዟቸዋል (ማቴ. ፲፯፥፩-፱፤ ማር.፱፥፪-፱)፡፡

በብሉይ ኪዳን ሊቀ ነቢያት ሙሴ ከእግዚአብሔር ጋር ሲነጋገር ቆይቶ ወደ ሕዝቡ ሲሔድ ፊቱ ያንጸባርቅ እንደ ነበርና የእስራኤላውያን ዓይን እንዳይጎዳ ሙሴ ፊቱን ይሸፍን እንደ ነበር ተጽፏል (ዘፀ. ፴፬፥፴፭)፡፡ ሙሴ የእግዚአብሔርን ድምፅ በመስማቱ ብቻ ፊቱ ያንጸባርቅ ከነበረ እግዚአብሔርን ፊት ለፊት በዓይን ተመልክቶ ብርሃኑን መቋቋምማ ምን ያህል ከባድ ይኾን?

እግዚአብሔር አምላክ በደብረ ታቦር ያደረገው መገለጥ በዘመነ ኦሪት ለሙሴ የሰጠውን ተስፋ ያስታውሰናል፡፡ ነቢዩ ሙሴ በዘመኑ ‹‹… አምላክነትህን (ባሕርይህን) ግለጽልኝ›› ሲል እግዚአብሔርን ተማጽኖት ነበር፡፡ እግዚአብሔርም ‹‹በባሕርዬ ፊቴን አይቶ የሚድን የለምና ፊቴን ማየት አይቻልህም እኔ በምገለጽልህ ቦታ ዋሻ አለና በብርሃን ሠረገላ ኾኜ እስካልፍ ድረስ በዋሻው ውስጥ ቁመህ ታየኛለህ፡፡ በባሕርዬ አይተህ ደንግጠህ እንዳትሞት በብርሃን ሠረገላ ኾኜ እስካልፍ ድረስ ቀዳዳ ባለው ዋሻ እሠውርሃለሁ፡፡ በብርሃን ሠረገላ ኾኜ ካለፍኹ በኋላ እጄን አንሥቼልህ ከወደ ኋላዬ ታየኛለህ እንጂ በባሕርዬ ግን ፊቴን ማየት አይቻልህም›› በማለት ለሙሴ ምላሽ ሰጥቶት ነበር፡፡ ይህም በፊት በፊት የሚጓዝ ሰው ኋላው (ጀርባው) እንጂ ፊቱ እንደማይታይ ጌታም በምልክት እንጂ በአምላክነቱ ለፍጡራኑ አለመገለጡን ያስረዳል፡፡ ምሥጢሩም አምስት ሺሕ ከአምስት መቶ ዓመት ሲፈጸም አምላክ ሰው ኾኖ ሥጋ ለብሶ በደብረ ታቦር በባሕርዩ እስኪገለጥለት ድረስ ሙሴ በመቃብር ተወስኖ እንደሚቆይ ያጠይቃል (ትርጓሜ ኦሪት ዘፀአት፣ ፴፫፥፲፫-፳፫)፡፡

እግዚአብሔር ‹‹ጀርባዬን ታያለህ›› ብሎ ለሙሴ በገባው ቃል መሠረት እነሆ በደብረ ታቦር በግርማ መለኮት፣ በክበበ ትስብእት (በለበሰው ሥጋ) ታየ፡፡ ነቢዩ ሙሴ ብርሃነ መለኮቱን በተመለከተ ጊዜም ‹‹ፊቴን ማየት አይቻልህም›› ያለው ቃሉ ይፈጸም ዘንድ የክርስቶስን ፊት ማየት አልተቻለውምና ወደ መቃብሩ ገባ፡፡ ኤልያስም ብርሃነ መለኮቱን አይቶ መቆም ስለ ተሳነው ወደ ብሔረ ሕያዋን ተመለሰ፡፡ የክርስቶስን መሞት በሥጋዊ ስሜት ተረድቶ ‹‹አይኹንብህ›› ያለው ቅዱስ ጴጥሮስ፤ መለኮታዊ ሥልጣንን የተመኙት ቅዱሳን ያዕቆብና ዮሐንስም አብሯቸው እየኖረ የማያውቁት ክርስቶስ የባሕርይ አምላክ መኾኑን በተረዱ ጊዜ ደንግጠው ወደቁ፡፡ እግዚአብሔር በደብረ ታቦር አንድነቱን፣ ሦስትነቱን ገለጠ፤ ከግርማ መለኮቱ የተነሣም ዓለም ተናወጠ፡፡

ጌታችን በዮርዳኖስ ሲጠመቅ የተገለጠው ምሥጢረ ሥላሴና የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት በደብረ ታቦር በገሃድ ተረጋግጧል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ የኾነው ደብረ ታቦር ምሥጢረ ሥላሴ ተገልጦበታል፤ የክርስቶስ አምላክነት ተመስክሮበታል፡፡ በደብረ ታቦር ብርሃነ መለኮቱ እንደ ተገለጠና የእግዚአብሔር አብ ምስክርነት እንደ ተሰማ ዅሉ ዛሬም በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ምሥጢረ ሥላሴ ሲነገር፣ የመለኮት ሥጋና ደም ሲታደል ይኖራል፡፡ በደብረ ታቦር ነቢያትም፣ ሐዋርያትም እንደ ተገኙ ዅሉ በቤተ ክርስቲያን ብሉይና ሐዲስ ኪዳን ይሰበካል፡፡ ሥርዓተ ቅዳሴ የሚፈጽሙ ልዑካን አምስት መኾናቸውም በደብረ ታቦር የተገኙትን ሙሴን፣ ኤልያስን፣ ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ዮሐንስን ያስታውሱናል፡፡ ዘወትር በቤተ መቅደሱ የሚፈተተው ኅብስትና የሚቀዳው ወይን ደግሞ በደብረ ታቦር የተገለጠው የጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋው፣ ክቡር ደሙ ነው፡፡

አንድም ደብረ ታቦር የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው፤ በደብረ ታቦር ነቢያትም ሐዋርያትም እንደ ተገኙ መንግሥተ ሰማያትንም ዅሉም ምእመናን በአንድነት ይወርሱታልና፡፡ ከመዓስባን ሙሴ፣ ከደናግል ኤልያስ መገኘታቸውም ደናግልም መዓስባንም በአንድነት ወደ መንግሥተ ሰማያትን እንደሚገቡ ያጠይቃል፡፡ አንድም ደብረ ታቦር የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክነቱንም ሰዉነቱንም በደብረ ታቦር እንደ ገለጠ ከእመቤታችን ከነፍስና ከሥጋዋ ጋር ተዋሕዶ ሰዉም አምላካም መኾኑን አሳይቷል፡፡ አምላክ ሰው፤ ሰውም አምላክ መኾኑ በድንግል ማርያም ማኅፀን ተገለጧል፡፡ በደብረ ታቦር ነቢያትም ሐዋርያትም እንደ ተገኙ እመቤታችንም የነቢያት ትንቢት ተፈጽሞባታል፤ የሐዋርያት ስብከት ጸንቶባታል፡፡ እርሷ አምላክን ለመሸከም ተመርጣለችና እመቤታችን በደብረ ታቦር ትመሰላለች፡፡ እንደዚሁም ደብረ ታቦር የአብያተ ጉባኤ (የአብነት ትምህርት ቤቶች) ምሳሌ ነው፡፡ በደብረ ታቦር የእግዚአብሔር ሦስትነት፣ አንድነት እንደ ታወቀ፤ ብርሃነ መለኮቱም እንደ ተገለጠ፤ ነቢያትና ሐዋርያትም እንደ ተገኙ ዅሉ በየአብነት ትምህርት ቤቶችም ምሥጢረ ሥላሴ፣ ነገረ መለኮት፣ ክብረ ቅዱሳን፣ ትንቢተ ነቢያትና ቃለ ወንጌል ዘወትር ይነገራል፣ ይሰበካል፤ ይተረጐማል፡፡

በአጠቃላይ ከጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዐበይት በዓላት መካከል አንደኛው የኾነው በዓለ ደብረ ታቦር እግዚአብሔር ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠበት በዓል በመኾኑ በቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ ነሐሴ ፲፫ ቀን በድምቀት ይከበራል፡፡ የአብነት ት/ቤት ደቀ መዛሙርትና ምእመናንም ብርሃነ መለኮቱን በደብረ ታቦር የገለጠ አምላክ ብርሃነ ምሥጢሩን በየልቡናቸው እንዲገልጥላቸው ለመማጸን ጸበል ጸሪቅ አዘጋጅተው ይዘክሩታል፡፡ ከዘመናት በፊት የተመኘውን የአምላኩን ፊት ከሙታን ተነሥቶ ለማየት የታደለው ሊቀ ነቢያት ሙሴ የተወለደውም በዚህች ዕለት ነው፡፡

እንዲህ እኛም በክርስቲያናዊ ምግባር ጐልምሰን፣ በትሩፋት ሥራ ከፍ ከፍ ብለን ከተገኘን በደብረ ታቦር እንደ ተደረገው ዅሉ በተቀደሰችው የእግዚአብሔር ተራራ በቤተ ክርስቲያን የሚፈጸሙ ምሥጢራትን ለመሳተፍ፣ የክርስቶስ ማደርያ በኾነችው በቅድስት ድንግል ማርያም እና ባለቤቱ ባከበራቸው በሌሎችም ቅዱሳን አማላጅነት ለመጠቀም፣ በየጉባኤ ቤቱ የሚቀርበዉን ጥበብ ለመቅሰም፣ በሚመጣው ዓለምም ሰማያዊ መንግሥቱን ለመውረስ እንበቃለን፡፡ አምላካችን በግርማ መለኮቱ ተገልጦ ለፍርድ በመጣ ጊዜ በቀኙ ያቆመን ዘንድም በክርስትና ሃይማኖት መጽናት፣ ትሕትናን ገንዘብ ማድረግ፣ በጥቅሉ በበጎ ምግባር መበርታት ይጠበቅብናል፡፡ ምሥጢረ መለኮቱን በደብረ ታቦር የገለጠ ጌታ ለእኛም መንፈሳዊውን አእምሮ፣ ማስተዋልና ጥበቡን ይግለጥልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ደብረ ታቦር አምሳለ ቤተ ክርስቲያን – ካለፈው የቀጠለ

በመምህር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

ነሐሴ ፲፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

እንደዚሁም ተራራ ሲወጡት አድካሚ እንደ ኾነ መንግሥተ ሰማያትም በብዙ ድካም ትወረሳለች፡፡ ‹‹እስመ በብዙኅ ጻማ ሀለወነ ንባእ ውስተ መንግሥተ እግዚአብሔር፤ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በብዙ መከራ እንገባ ዘንድ አለን›› እንዲል (ሐዋ. ፲፬፥፳፫)፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃነ መለኮቱን በደብረ ታቦር የገለጸበት ምክንያት ምሥጢር በብዙ ድካም እንጂ ምንም ሳይደክሙ እንደማይገኝ ሲገልጽ ነው፡፡ ለደቀ መዛሙርቱ ብዙዎቹን ምሥጢራት የገለጠላቸው ከከተማ ውጭ ነው፡፡ ቀደም ሲልም ለሙሴ የቃል ኪዳኑን ጽላት ሲሰጠው ወደ ሲና ተራራ በመጥራት ነበር፡፡ ነገረ ሥጋዌዉንም በነበልባልና በእሳት አምሳል የገለጠለት በኮሬብ ተራራ በጎቹን አሰማርቶ በነበረበት ጊዜ እንደ ኾነ መጻሕፍት ይመሰክራሉ (ዘፀ. ፫፥፩)፡፡

ምሥጢር ይገለጥልን ባላችሁ ጊዜ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገስግሱ፤ ቤተ ክርስቲያንን ደጅ ጽኑ ለማለት ጌታችን ምሥጢሩን በተራራ ገለጠ፡፡ ወደ ተራራው ሲወጣም ስምንቱን ደቀ መዛሙርቱን ከይሁዳ ጋር ከተራራ እግር ሥር ትቶ ሦስቱን አስከትሎ ወጥቷል፡፡ ለሦስቱ በተራራው ላይ የተገለጠው ድንቅ ምሥጢርም ከእግረ ደብር ላሉት በሳምንቱ ተገልጧል፤ ከይሁዳ በቀር፡፡ ለዚህ ምሥጢር ብቁ ያልነበረው ይሁዳ ብቻ ነው፡፡ ይህም ተገቢውን ምሥጢር ለተገቢው ሰው መንገር እንደሚገባ፤ ለማይገባው ደግሞ ከመንገር መቆጠብ ተገቢ እንደ ኾነ ያስተምረናል፡፡ ‹‹እመኒ ክዱን ትምህርትነ ክዱን ውእቱ ለሕርቱማን ወለንፉቃን …፤ ወንጌላችን የተሰወረ ቢኾንም እንኳን የተሰወረባቸው ለሚጠፉት ነው፡፡ እግዚአብሔርን የሚመስለው የክርስቶስ የክብሩ ወንጌል ብርሃን እንዳያበራላቸው የዚህ ዓለም አምላክ ልባቸውን አሳውሯልና፤›› (፪ኛ ቆሮ. ፬፥፫-፭) በማለት ሐዋርያው የሰጠው ትምህርትም ይህን መሰል ምሥጢር ለሚገባው እንጂ ለማይገባው ሰው መግለጥ ተገቢ አለመኾኑን የሚያስረዳ ነው፡፡

፪ኛ የድል ተራራ ስለ ኾነ

ነቢዪቱ ዲቦራ የእስራኤል ጠላት የነበረው የኢያቢስን የሠራዊት አለቃ ሲሣራን ለመውጋት ወደ ደብረ ታቦር ዐሥር ሺሕ ሰዎችን አስከትሎ እንዲወጣ ለባርቅ ነግራዋለች (መሳ. ፬፥፮)፡፡ በዚህ መልኩ ባርቅ ዐሥር ሺሕ ሰዎችን አሰልፎ ዲቦራን አስከትሎ በደብረ ታቦር ሰፍሮ የነበረውን የሲሣራን ሠራዊት ድል ነሥቶበታል፡፡ ሲሣራ ዘጠኝ መቶ የብረት ሠረገላ እንደዚሁም ብዙ ሠራዊት በታቦር ያሰለፈ ቢኾንም ድል ግን ረድኤተ እግዚብሔርን ጥግ ላደረገው ለባርቅ ኾነ፡፡ በዚህ ጊዜ ዲቦራ በታቦር ተራራ የሙሴ እኅት ማርያም በኤርትራ ባሕር የዘመረችውን መዝሙር የመሰለ ምስጋና አቅርባለች፡፡ ዅሉም እስራኤላውያን የድል መዝሙር ዘምረውበታል፤ ፈጣሪአቸውን አመስግነውበታል፡፡ ጌታችንም የባሕርይ አምላክነቱን ገልጾ ከደቀ መዛሙርቱ ልቡና አጋንንትን የሚያባርርበት ዲያብሎስን ድል የሚነሳበት ስለኾነ ከሌሎች ተራሮች ተመርጧል፡፡

፫ኛ ትንቢት ስለ ተነገረለት

‹‹ታቦር ወአርሞንኤም በስመ ዚአከ ይትፌሥሑ ወይሴብሑ ለስምከ፤ ታቦርና አርሞንኤም በስምህ ደስ ይላቸዋል፤›› (መዝ. ፹፰፥፲፪) ብሎ ከክርስቶስ ሰው ኾኖ መገለጥ በፊት አምላካችን ክርስቶስ ብርሃነ መለኮቱን በደብረ ታቦር እንደሚገልጽ፣ ብርሃኑ ከደብረ ታቦር እስከ አርሞንኤም ድረስ እንደሚታይ፣ ይህም መለኮታዊ ብርሃን በታቦርና በአርሞንኤም ዙሪያ ለነበሩ ሕዝቦች ደስታ እንደሚኾን ቅዱስ ዳዊት ተናግሯል፡፡ ታቦር የተባለው ተራራ ከገሊላ ባሕር በምዕራብ በኩል በ፲ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኝ ሲኾን ተራራው እስከ ፭፻፸፪ ሜትር ከባሕር ጠለል (ወለል) ከፍ ይላል፡፡

ቀደም ሲል እንደገለጽነው ባርቅ ሲሣራን ድል ነስቶበታል፤ የመጀመሪያው የእስራኤል ንጉሥ ሳዖል በሳሙኤል እጅ ተቀብቶ ሲመለስ ‹‹ሦስት ሰዎች ታገኛለህ አንዱ ሦስት የድል ጠቦቶች፣ ሁለተኛው ሦስት ዳቦ ይዟል፤ ሦስተኛውም የወይን ጠጅ አቆማዳ ይዟል፡፡ ሰላምታ ይሰጡሃል›› ብሎ ሳሙኤል ነግሮት ነበር፡፡ በነገረው መሠረት ሦስት ሰዎችን አግኝቶበታል (፩ኛ ሳሙ. ፲፥፫-፭)፡፡ ስለዚህ ተራራ ቅዱስ ዳዊት በድጋሜ እንዲህ በማለት ትንቢት ተናግሮለታል፤ ‹‹የእግዚአብሔር ተራራ የለመለመ ተራራ ነው፡፡ የጸና ተራራ የለመለመ ተራራ ነው፡፡ እግዚአብሔር ይህን ተራራ ያድርበት ዘንድ ወደደው›› (መዝ. ፷፯፥፲፭) ብሎ እግዚብሔር ብርሃነ መለኮቱን እንደሚገልጥበት ዘምሮአል፡፡ በእነዚህ ከላይ በአየናቸው ሁለት ምክንያት ደብረ ታቦር ለዚህ ምሥጢር ተመርጧል፡፡

ጌታችን ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠው በምን ምክንያት ነው?

ነሐሴ ሰባት ቀን በቂሣርያ ደቀ መዛሙርቱን ‹‹ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል?›› ብሎ በጠየቃቸው ጊዜ ‹‹ኤርምያስ ነው፤ ኤልያስ ነው፤ ዮሐንስ መጥምቅ ነው፤ ከነቢያት አንዱ ነው ይሉሃል›› የሚል የተለያየ መልስ ሰጥተዉት ነበር፡፡ ‹‹እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ?›› ባላቸው ጊዜም ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ›› ብሎ መስክሯል፡፡ ስለዚህ ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን የገለጠው በሦስት ምክንያት ነው፤

፩ኛ በፍጡር ቃል የተመሰከረውን እውነት በባሕርይ አባቱ ለማስመስከር፤

፪ኛ ‹‹ከነቢያት አንዱ ነው›› ብለውት ነበርና እግዚአ ነቢያት (የነቢያት ጌታ) እንደ ኾነ ለማስረዳት፤

፫ኛ ክርስቶስ ‹‹እሰቀላለሁ፤ እሞታለሁ›› ባለ ጊዜ፣ ጴጥሮስ ‹‹ሐሰ ለከ፤ ልትሞት አይገባህም›› ብሎት ነበርና ‹‹እርሱን ስሙት›› የሚለዉን የእግዚአብሔር አብን መልእክት ለማሰማት፡፡

በፍጡሩ በጴጥሮስ የተመሰከረውን ምስክርነት የባሕርይ አባቱ ‹‹ይህ የምወደው ልጄ ነው፤ እርሱን ስሙት›› ማለት ‹‹‹እሞታለሁ፤ እሰቀላለሁ› ቢላችሁ ‹አይገባህም› አትበሉት፡፡ ዓለም የሚድነው በእርሱ ሞት ነውና ተቀበሉት›› ለማለት ነው፡፡ ‹‹ይህ ሊኾንብህ አይገባም›› ብሎት ነበርና ለጴጥሮስ መልስ እንዲኾን፡፡ ያዕቆብና ዮሐንስም ‹‹አንዳችን በቀኝህ አንዳችን በግራህ እንሾም›› ብለው ነበርና ፍቅረ ሲመትን ሊያርቅላቸውና የእርሱን የባሕርይ ክብሩን አይተው የመጣለት ዓላማ ልዩ መኾኑን እንዲረዱ ሲያደርጋቸው እነዚህን ሦስቱን ይዞ ወደ ተራራው ወጥቷል፡፡ ‹‹ከነቢያት አንዱ ነው›› ብለውት ነበርና ከነቢያት ሙሴንና ኤልያስን በተራራው ተገኝተው እንዲመሰክሩ አድርጓል፡፡ ሙሴ ‹‹የእኔ የሙሴን አምላክ ‹ሙሴ› የሚልህ ማነው? አምላከ ሙሴ፣ እግዚአ ሙሴ ይበሉህ እንጂ››፤ ኤልያስም ‹‹የእኔን አምላክ ‹ኤልያስ› የሚልህ ማነው? አምላከ ኤልያስ፣ እግዚአ ኤልያስ ይበሉህ እንጂ›› በማለት መስክረውለታል፡፡

ጌታችን ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠው እንዴት ነው?

ይህን ጥያቄ ለማብራራትም ኾነ ለመተንተን ዕውቀትም ቃላትም ያጥረናል፡፡ ወንጌላውያን መግለጥ በሚችሉት መጠን ከገለጹት ያለፈ ልናብራራው የምንችለው አይደለም፡፡ ማቴዎስ እንዲህ ይገልጸዋል፤ ‹‹ወተወለጠ ራዕዩ በቅድሜሆሙ ወአብርሀ ገጹ ከመ ፀሐይ ወአልባሲሁኒ ኮነ ፀዐዳ ከመ በረድ፤ በፊታቸውም ተለወጠ፡፡ ፊቱም እንደ ፀሐይ በራ፤ ልብሱም እንደ ብርሃን ነጭ ኾነ፤›› (ማቴ. ፲፯፥፪)፡፡ ወንጌላዊው በዚህ ዓይነት መንገድ የገለጸው ምሳሌ ስላጣለት ነው፡፡ ማርቆስም ይህንኑ ኃይለ ቃል ተጋርቶ ‹‹ልብሱም አንፀባረቀ፤ አጣቢም በምድር ላይ እንደዚያ ሊያነጣው እስከማይችል በጣም ነጭ ኾነ፤›› (ማር. ፱፥፪) በማለት ሲገልጸው፣ ሉቃስም በተመሳሳይ መልኩ ‹‹የፊቱ መልክ ተለወጠ፤ ልብሱም ተብለጭልጮ ነጭ ኾነ›› ሲል ገልጾታል (ሉቃ. ፱፥፳፱-፴)፡፡ እኛም ከዚህ ወንጌላውያን ከገለጹበት መንገድ የሚሻል ምሳሌ አናገኝለትም፡፡

ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን በደብረ ታቦር በገለጠ ጊዜ ፊቱን ማየት ተስኗቸው ነቢያት ወደየመጡበት መመለሳቸውን ሲያመላክቱ ኢትዮጵያዊቷ የቅኔ መምህርት እማሆይ ገላነሽ በቅኔአቸው እንዲህ በማለት አመሥጥረውታል፤

‹‹በታቦርሂ አመ ቀነፀ መለኮትከ ፈረስ

ኢክህሉ ስሒቦቶ ሙሴ ወኤልያስ››

ትርጕሙም፡- ‹‹መለኮት ፈረስህ በደብረ ታቦር በዘለለ ጊዜ ሙሴና ኤልያስ ሊስቡት አልቻሉም›› ማለት ሲኾን፣ ይህም ክርስቶስ በምን ዓይነት ግርማ እንደ ተገለጸ ያስረዳል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ደብረ ታቦር አምሳለ ቤተ ክርስቲያን – የመጀመርያ ክፍል

በመምህር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

ነሐሴ ፲፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹ወኮነት ደብረ ታቦር አምሳለ ቤተ ክርስቲያን እስመ አስተጋብአት እም ብሉይ ወሐዲስ፤ ደብረ ታቦር የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ነች፤ ከብሉይና ከሐዲስ ሰብስባለችና፡፡›› ምክንያቱም ከብሉይ ኪዳን ነቢያት ሙሴና ኤልያስን፤ ከሐዲስ ኪዳን ሐዋርያት ጴጥሮስን ያዕቆብን፣ ዮሐንስን ከመምህራቸው ከክርስቶስ ጋር ሰብስባለችና፡፡ ደግሞም ቤተ ክርስቲያን የተመሠረተችው በነቢያትና ሐዋርያት መሠረትነት ነውና፡፡ ‹‹እስመ ተሐነጽክሙ ዲበ መሠረተ ነቢያት ወሐዋርያት እንዘ ክርስቶስ ርዕሰ ማዕዘንተ ሕንጻ፤ በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል፤ የማዕዘኑም ራስ ደንጋይ ክርስቶስ ነው፤›› እንዲል (ኤፌ. ፪፥፳)፡፡

በዓለ ደብረ ታቦር

እንደሚታወቀው በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘጠኙ ዐበይት በዓላት አንዱ በዓለ ደብረ ታቦር ነው፡፡ በዓሉ ከዐበይት በዓላት የተመደበበት ምክንያትም በደብረ ታቦር የተገለጸው ምሥጢር ድንቅ በመኾኑ ነው፡፡ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ አንድ አንድ ጊዜ ለዅሉም፤ አንድ አንድ ጊዜ ደግሞ በከፊል ምሥጢራትን ገልጾላቸዋል፡፡ ከእነዚህ ምሥጢራትም የሚከተሉት ተጠቃሾች ናቸው፤ ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን በቤተ አልዓዛርና በቤተ ኢያኢሮስ፤ ምሥጢረ ቍርባንን እንደዚሁ በአልዓዛር ቤት፤ ነገረ ምጽአትን በደብረ ዘይት ገልጿል (ማቴ. ፱፥፳፫፤ ፳፮፥፳፮፤ ዮሐ. ፲፩፥፵፫)፡፡

ከእነዚህ ከላይ ከተዘረዘሩት ምሥጢራት መካከል ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንና ምሥጢረ ቊርባንን ዅሉም ደቀ መዛሙርት ያዩ ሲኾን ነገረ ምጽአትን ግን በከፊል ጴጥሮስ፣ ያዕቆብና ዮሐንስ አራተኛ እንድርያስን ጨምረው ተረድተዋል፡፡ የደብረ ታቦርን ምሥጢር ከዚህ ልዩ የሚያደርገው ከሐዋርያት ጴጥሮስ፣ ዮሐንስና ያዕቆብ ብቻ መገኘታቸው፤ ከነቢያት ደግሞ ሙሴና ኤልያስ መጨመራቸው ነው፡፡ ከጌታችን ዘጠኝ በዓላት አንዳንዶቹ በተፈጸመው ድርጊት የተሰየሙ ሲኾን ከፊሎቹ ድርጊቱ በተፈጸመባቸው ቦታዎች ተሰይመዋል፡፡ በድርጊቱ የተሰየሙት ፅንሰት፣ ልደት፣ ጥምቀት፣ ስቅለት፣ ትንሣኤ፣ ዕርገት ሲኾኑ ሁለቱ ሆሣዕና እና ጰራቅሊጦስ ደግሞ ድርጊትንና ስምን አስተባብረው የያዙ ናቸው፡፡ ከእነዚህ ዅሉ ተለይቶ ደብረ ታቦር ድርጊቱ በተፈጸመበት ቦታ ተሰይሟል፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከዅሉም ምሥጢራት ነገረ ምጽአቱንና ምሥጢረ መንግሥቱን በተራራ ላይ ገልጿል፡፡ ነገረ ምጽአትን በደብረ ዘይት የገለጸበትን ምክንያት ጠቢቡ ሰሎሞን ‹‹ለዅሉም ጊዜ አለው›› እንዳለው ለጊዜው ትተነው ወደ ደብረ ታቦር እንመለስ፤ ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን ለደቀ መዛሙርቱ የገለጠበት፤ ነቢያት ሊያዩት የተመኙትን ያዩበት ነቢያትና ሐዋርያት በአንድነት የተገናኙበት፤ ተገናኝተውም እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ኾነው የክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት የመሰከሩበት፤ እግዚአብሔር ወልድ በክበበ ትስብእትና በግርማ መለኮት የተገለጠበት፤ እግዚአብሔር አብ በደመና ‹‹የምወደው ለተዋሕዶ የመረጥኩት በእርሱ ህልው ኾኜ የምመለክበት ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት፤›› ብሎ የመሰከረበት፤ መንፈስ ቅዱስም በአምሳለ ርግብ የወረደበት፤ እግዚአብሔር አንድነቱን፣ ሦስትነቱን የገለጠበት እነ ቅዱስ ጴጥሮስ ለመኖር የተመኙት ደብረ ታቦር ነው፡፡ በዓሉ የጌታችን ሲኾን በስሙ ደብረ ታቦር ተብሏል፡፡ ይህ በዓል ያን ጊዜ ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን አስከትሎ ወደ ተራራው ሲወጣ፣ በተራራው ራስ ላይ ምሥጢሩን ሲገልጥላቸው፣ አእምሮአቸውን ሲከፍትላቸው፣ ከግርማው የተነሣ ፈርተው ሲወድቁና ሲያነሣቸው በዐይነ ሕሊናችን የምንመለከትበት በዓል ነው፡፡

ጌታችን ወደ ደብረ ታቦር የወጣው መቼ ነው?

ወንጌላዊያኑ ቅዱስ ማቴዎስና ቅዱስ ማርቆስ ጌታችን ምሥጢረ መለኮቱን ለመግለጥ ወደ ደብረ ታቦር የወጣው ደቀ መዛሙርቱን በቂሣርያ ‹‹ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል?›› ብሎ በጠየቃቸው በሰባተኛው ቀን እንደ ኾነ ጽፈዋል፡፡ ቅዱስ ሉቃስ ደግሞ በስምንተኛው ቀን ነው ይላል፡፡ (ማቴ. ፲፯፥፩-፰፤ ማር. ፱፥፪-፰፤ ሉቃ. ፱፥፳፰)፡፡ ነገሩ እንዴት ነው? ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ማቴዎስ በጠቀሰው በሰባተኛው ቀን መኾኑን በትርጓሜያቸው አስቀምጠዋል፡፡ ታዲያ ስለ ምን ስምንት አለ? የሚለውን ሲያትቱ (ሲያብራሩ) ስምንት ያለው ሰባት ሲል ነው ብለው ተርጕመውታል፡፡ ምክንያቱም አንድ ሳምንት የሚባለው ሰባት ቀን ነው፡፡

ሊቁ ቅዱስ አትናቴዎስ ስለ ዕለተ ሰንበት ሲናገር ‹‹ኦ ቅድስት ንዒ ኀቤነ ለለሰሙኑ ከመ ንትፈሣ ብኪ ለዓለመ ዓለምቅድስት ሆይ በየሳምንቱ ወደኛ ነዪ ለዘለዓለሙ በአንቺ ደስ ይለን ዘንድ፤›› በማለት መናገሩ ሰሙን ማለት ሳምንት እንደ ኾነ ያጠይቃል፡፡ ሳምንት ማለት ደግሞ ሰባት ቀን ነው፡፡ ከዚህ የተነሣ ሉቃስ በስምንተኛው ቀን ያለው በሳምንቱ (በሰባተኛው ቀን) ሲል ነው፡፡ በሌላ መልኩ ማቴዎስ በሰባተኛው ቀን ሲል ሉቃስ በስምንተኛው ቀን ማለቱ የወጡበትንና የተመለሱበትን ቈጥሮ ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ መጽሐፍ የጎደለውን ሞልቶ፣ የሞላውን አትርፎ መናገር ልማዱ ነው፡፡ ይህንም በሚከተሉት ኃይለ ቃላት መረዳት እንችላለን፤

  • ሰሎሞን ‹‹ወነበርኩ ውስተ ከርሠ እምየ ዐሠርተ አውራኃ ርጉዐ በደም፤ በእናቴ ማኅፀን በደም ረግቼ ዐሥር ወር ነበርኹ፤›› ብሏል (ጥበ. ፯፥፪)፡፡ የእናቶች እርግዝና ጊዜ ዘጠኝ ወር ኾኖ ሳለ ጠቢቡ ዐሥር ወር ተቀመጥሁ አለ፡፡ ይህን ያኽል ረጅም ቀን የመጨመር ልማድ ያለው መጽሐፍ ‹‹በስምንተኛው ቀን›› ቢል ብዙ የሚደንቅ፣ የሚጣረስም አይደለም፡፡ የሚጣረሰው ወይም የሚጋጨው የእኛ አእምሮ ነው፤ የዕውቀት ማነስ ስላለብን፡፡
  • ‹‹ወበጽሐ ወር ለኤልሳቤጥ፤ የኤልሳቤጥም የመውለጃዋ ወራት ደረሰ›› (ሉቃ. ፩፥፶፯) ሲል ቀን አልጠቀሰም፡፡ ሰው የሚወለድበት ቀኑ የታወቀ ስለ ኾነ ነው፡፡
  • ስለ እመቤታችን ሲናገር ‹‹በዚያ ሳሉም የመውለጃዋ ወራት ደረሰ የበኵር ልጅዋንም ወለደች›› ብሏል (ሉቃ. ፪፥፮)፡፡ ከአንድ በላይ የኾኑ ወሮች ‹‹ወራት›› ይባላሉ፡፡

ይህ ዅሉ የመጻሕፍት ቃል መጽሐፍ ሲያሻው ጠቅልሎ፣ ሲፈልግ ዘርዝሮ፣ አስፈላጊ ሲኾን ደግሞ በአኀዝ ወስኖ፣ ደግሞም አጕድሎ፣ እንደዚሁም ሞልቶ ሊናገር እንደሚችል ያስረዳናል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በድንግል ማርያም ማኅፀን ያደረው ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ሲኾን መጽሐፍ ‹‹ተፀውረ በከርሣ ፱ተ አውራኃ፤ ዘጠኝ ወር በማኅፀኗ አደረ›› በማለት አምስት ቀን አጕድሎ ሲናገር እናገኘዋለን፡፡ ከዚህ አንጻር ሉቃስም አንድ ቀን ጨምሮ ተናግሯል፡፡ መጨመርም ማጕደል የመጻሕፍት ልማድ ነውና፡፡

ለዚህ ምሥጢር ደብረ ታቦር ለምን ተመረጠ?

፩ኛ ምሳሌነት ስላለው

የታቦር ተራራ፣ የቤተ ክርስቲያን፤ የወንጌል እና የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው፡፡ አንደኛውን ምሳሌ ከላይ የተመለከትን ሲኾን ሁለተኛው ምሳሌ አበው በትርጓሜአቸው እንዲህ አብራርተውታል፤ ተራራ ሲወጡት አድካሚ ነው፤ ከወጡት በኋላ ግን ዅሉንም ቁልጭ አድርጎ ሲያሳይ ደስ ያሰኛል፤ ወንጌልም ሲማሯት፤ ሲያስተምሯት ታደክማለች፤ ከተማሯት በኋላ ግን ጽድቅና ኀጢአትን፤ እውነትንና ሐሰትን ለይታ ስታሳውቅ ደስ ታሰኛለችና፡፡ በሌላ መልኩ ከተራራ ላይ ያለ ሰው ጠላቱን በቀላሉ በአፈር በጠጠር ድል መንሳት፣ ፍትወታት እኩያትን ማሸነፍ ይችላል፡፡ ከተራራ ላይ መሰወር እንደማይቻል በወንጌል ያመነ ሰውም ተሰውሮ አይቀርም፤ በመልካም ሥራው ለዅሉም ይገለጣል፡፡ በሦስተኛውም ተራራ የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው፡፡ ከነቢያት ሁለቱ ከሐዋርያት ሦስቱ በተራራው ላይ መገኘታቸው መንግሥተ ሰማያት ነቢያትም ሐዋርያትም በአንድነት የሚወርሷት መኾኗን ያስረዳል፡፡ ከደናግላን ኤልያስና ዮሐንስ፣ ከመዓስባን (በሕግ ጋብቻ ኖረው ሚስቶቻቸው የሞቱባቸው ወይም ትዳራቸውን የተዉ) ሙሴና ጴጥሮስ በተራራው ላይ መገኘታቸውም መንግሥተ ሰማያት ደናግላንም መዓስባንም መልካም ሥራ ሠርተው በአንድነት የሚወርሷት እንደ ኾነች ይገልጻል፡፡

ይቆየን

ዘመነ ክረምት – ክፍል አምስት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! በክፍል አራት ዝግጅታችን ከነሐሴ ፲ እስከ ፳፯ ቀን (ከማኅበር እስከ አብርሃም) ድረስ ያለው ሦስተኛው የዘመነ ክረምት ክፍለ ጊዜ (ንዑስ ክፍል) ‹ዕጕለ ቋዓት፣ ደሰያት፣ ዓይነ ኵሉ› እንደሚባል፤ ይኸውም የሰው ልጅ ብቻ ሳይኾን የሰማይ አዕዋፍ፣ የምድር አራዊትና እንስሳትም ጭምር እግዚአብሔርን አምነው በተስፋ መኖራቸው የሚዘከርበት፣ ደሴቶች በልምላሜ ማሸብረቃቸው የሚነገርበት ክፍለ ክረምት እንደ ኾነ፤ በቤተ ክርስቲያን የሚነገረው ቃለ እግዚአብሔርም በእነዚህ ምሥጢራት ላይ እንደሚያተኩር አስታውሰን፣ በተለይ ዕጕለ ቋዓትን መነሻ አድርገን ወቅቱን የሚመለከት ትምህርት አቅርበን ነበር፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን ደግሞ ባለፈ ካረፍንበት እንቀጥላለን፡፡ መልካም ንባብ! 

ደሰያት

በውኃ የተከበበ የብስ መሬት ‹ደሴት› ይባላል፤ ‹ደሰያት› ደግሞ ብዙ ቍጥርን አመላካች ቃል ነው፡፡ በዚህ ወቅት ስለ ደሴቶች በስፋት ይነገራል፡፡ ወቅቱ በድርቅ ብዛት የተጎዱ ደሴቶች በውኃ ብዛት የሚለመልሙበት፤ በውስጣቸው የሚኖሩ ሰዎች ብቻ ሳይኾኑ እንስሳትም አዕዋፍም ጭምር በሚበቅለው እኽልና በሚያገኙት ምግብ የሚደሰቱበት ጊዜ ነው፡፡ ደሴቶች በውኃ የተከበቡ የመሬት ክፍሎች እንደ መኾናቸው በዚህ ወቅት በልምላሜ ቢያጌጡም በማዕበልና በሞገድ መቸገራቸውም አይቀርም፡፡ ይህም የቤተ ክርስቲያን (የምእመናን ሕይወት) እና የዓለም ምሳሌ ነው፡፡ ደሴቶች በውኃ መከበባቸው ቤተ ክርስቲያን (የምእመናን ሕይወት) በክርስቶስ ደም የተመሠረተች፤ በቃለ እግዚአብሔር የታነጸች ለመኾኗ፤ ደሴቶች በማዕበልና በሞገድ መናወጣቸው ደግሞ በዓለም ውስጥ የሚከሠቱ ረኃብ፣ ጥላቻ፣ ጦርነት፣ ወዘተ የመሳሰሉ ችግሮች፤ በተለይ ሰይጣን የሚያመጣቸው ልዩ ልዩ ኅብረ ኃጢአት (የኀጢአት ዓይነቶች) የቤተ ክርስቲያንን (የምእመናንን) ህልውና የሚፈታተኑ መሰናክሎች መኾናቸውን ያጠይቃል፡፡

ይህቺ ዓለም፣ በውኃ የምትመሰል፣ ሞገድና ማዕበል የበዛባት ሥፍራ ናት፤ የክርስትና ሕይወት ደግሞ በውኃ የተከበበ መሬት፡፡ ውኃ በሞገድ፣ በማዕበል እንደሚናወጥ ዅሉ፣ ዓለምም በተፈጥሮም ይኹን በሰው ስሕተት በሚመጣ ኑፋቄ፣ ክህደት፣ መከራ፣ ችግር፣ ረኃብ፣ ጦርነት ትናወጣለች፤ ትንገላታለች፤ ትሰቃያለች፤ ትፈተናለች፡፡ ዛሬ በዓለም ላይ እየተፈጸመ ያለው ሰይጣናዊ ድርጊት ዅሉ ለዚህ ማስረጃ ነው፡፡ ዓለም ፈተና ላይ ናት፡፡ አልጠግብ ባይነት፣ ትምክህተኝነት፣ እኔ እበልጥ ባይነት፣ ፍቅር አልባነት (ጥላቻ)፣ ትዕቢት፣ ክህደት፣ ጥርጥር፣ ወዘተ የመሳሰሉ ችግሮች በነዋሪዎቿ ዘንድ እየተስፋፉ በመምጣታቸው ዓለም በፈተና ሞገድ እየተናወጠች ነው፡፡ እርሱ በቸርነቱ ሞገዱና ማዕበሉ ጸጥ እንዲል ካላደረገ የሰው ጥበብና ጥረት ብቻ ከዚህ ፈተና ዓለምን ሊያወጣት አይችልም፡፡ በውኃ የተከበበ መሬት ሞገድ፣ ማዕበልና ስጥመት እንደሚያጋጥመው ዅሉ፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም (የክርስትና ሕይወትም) በልዩ ልዩ መከራና ፈተና የታጀበ ነው፡፡ ምክንያቱም ክርስቲያኖች የምንኖረው ፈተና በሚያናውጣት ዓለም ወይም ውጣ ውረድ በበዛባት ምድር ላይ ነውና፡፡ ይኸውም ኀጢአት፣ ስደት፣ ኀዘን፣ ረኃብ፣ በሽታ፣ ጦርነት፣ ወዘተ. የመሳሰሉትን ምድራዊ ችግሮች ዅሉ ያካትታል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹እንዲህም ያለ መከራ በዓለም ባሉ ወንድሞቻችሁ ዅሉ እንደሚፈጸም ዕወቁ›› በማለት እንዳስተማረው (፩ኛ ጴጥ. ፭፥፱) በመላው ዓለም የሚኖሩ ክርስቲያኖች ዛሬ በመከራ ውስጥ ናቸው፡፡ በአንድ በኩል የዓለም የኑሮ ሸክም ከብዷቸው ይሰቃያሉ፤ በሌላ በኩል ደግሞ በአሕዛብና በአረማውያን ዛቻና ማስፈራሪያ ይጨነቃሉ፡፡ የክርስትና ትርጕም የገባቸውም በፈቃዳቸው በሰማዕትነት ይሞታሉ፡፡ ይህን ዅሉ ፈተና ተቋቁሞ በክርስትና ሃይማኖት ጸንቶ፣ በምግባር በርትቶ፣ በጸሎት ተግቶ የሚኖር ምእመን እርሱ ብፁዕ ነው፡፡ በሰማያዊው የእግዚአብሔር መንግሥት ለጻድቃን የተዘጋጀውን ሰላማዊና ዘለዓለማዊ ማረፊያ ይወርሳልና፡፡ እንግዲህ እኛም ሞገዱና ማዕበሉ ማለትም ምድራዊ ውጣ ውረዱና ፈተናው ቢያንገላታንም በዚህ ዓለም የሚጎድልብንን ሥጋዊው ጥቅምና የሚደርስብንን ጊዜያዊ መከራ ሳይኾን በእውነተኛው አገራችን በሰማይ የምንወርሰውን ዘለዓለማዊ መንግሥት ተስፋ በማድረግ ዅሉንም በጸጋ እንቀበል፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም ሃይማኖታችንንና ቤተ ክርስቲያናችንን ከልዩ ልዩ ፈተና ይጠብቅልን ዘንድም በፍጹም ሃይማኖት ኾነን እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹ከስጥመት አድነን?›› እያልን እግዚአብሔርን በጸሎት እንጠይቀው፡፡ እርሱ በባሕር፣ በሞገድ፣ በማዕበልና በነፋስ የሚመሰለውን የዓለምን ውጣ ውረድና መከራ መገሠፅ፤ ሁከቱንም ጸጥ ማድረግ የሚቻለው አምላክ ነውና (ማቴ. ፰፥፳፫-፳፯)፡፡ ከዓቅማችን በላይ የኾነ ችግር ሲያጋጥመን ደግሞ የሚያስጨንቀንን ጉዳይ ዅሉ ለእርሱ ለፈጣሪያችን እንስጠው፡፡ ይህን ለመወሰን እንዲቻለንም የሚከተለውን የመጽሐፍ ቅዱስ ኃይለ ቃል እናስተውል፤ ‹‹እንግዲህ በጐበኛችሁ ጊዜ ከፍ ከፍ ያደርጋችሁ ዘንድ ከጸናችው ከእግዚአብሔር ክንድ በታች ራሳችሁን አዋርዱ፡፡ እርሱ ስለ እናንተ ያስባልና የሚያስጨንቃችሁን ዅሉ በእርሱ ላይ ጣሉት፡፡ እንግዲህ ዐዋቂዎች ኹኑ፤ ትጉም፡፡ ጠላታችሁ ጋኔን የሚውጠውን ፈልጎ፣ እንደሚያገሳ አንበሳ ይዞራልና፡፡ እርሱንም በእምነት ጸንታችሁ ተቃወሙት፤ እንዲህም ያለ መከራ በዓለም ባሉ ወንድሞቻችሁ ዅሉ እንደሚፈጸም ዕወቁ፡፡ ፍቅርንም አጽንታችሁ ያዙአት፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዘለዓለም ክብሩ የጠራችሁ የጸጋ ዅሉ አምላክ ለጥቂት ጊዜ መከራን ከተቀበላችሁ በኋላ ፍጹማን ያደርጋችኋል፤ ያጸናችኋል፤ ልባሞችም ያደርጋችኋል፤›› (፩ኛ ጴጥ. ፭፥፮-፲)፡፡

ዓይነ ኵሉ

‹ዓይነ ኵሉ› ትርጕሙ በግእዝ ቋንቋ ‹የዅሉም ዓይን› ማለት ነው፡፡ ይህ ወቅት ያለፈው (በበጋ የነበረው) እኽል ከሪቅ፣ ከጎተራ ያለቀበት፤ የተዘራውም ያላፈራበት ገና የተክል ጊዜ ነው፡፡ ፍጥረታት በሙሉ የፍሬውን ሰዓት በተስፋ የሚጠባበቁበት ክፍለ ክረምት ስለ ኾነ ወቅቱ ‹ዓይነ ኵሉ› ተብሏል፡፡ ይኸውም ፍጥረታት ዅሉ ወደ ፈጣሪያቸው ወደ እግዚአብሔር በማንጋጠጥ የዕለት ጕርስ፣ የዓመት ልብስ እንዳይከለክላቸው እንደሚማጸኑና ዘወትር የእርሱን መግቦት ተስፋ አድርገው እንደሚኖሩ የሚያስረዳ ቃል ነው፡፡ ‹‹ዐይነ ኵሉ ነፍስ ይሴፎ ኪያከ አንተ ትሁቦሙ ሲሳዮሙ በጊዜሁ ትሰፍሕ የማነከ ወታጸግብ ለኵሉ እንስሳ ዘበሥርዓትከ፤ የሰው ዅሉ ዓይን አንተን ተስፋ ያደርጋል፤ አንተም ምግባቸውን በየጊዜው ትሰጣቸዋለህ፡፡ ቀኝ እጅህን ትዘረጋለህ፤ በሥርዓትህ ለሚኖሩ እንስሳት ዅሉ ታጠግባለህ፤›› እንዳለ ቅዱስ ዳዊት (መዝ. ፻፵፬፥፲፭-፲፮)፡፡ ይኸውም የሰው ልጅ ዅሉ (ዓይን የተባለ ሰውነት ነው) እግዚአብሔርን ተስፋ አድርጎ እንደሚኖር፤ እርሱም በዘር ጊዜ ዘሩን፣ በመከር ጊዜ መከሩን፣ በበልግ ጊዜ በልጉን እያዘጋጀ በየጊዜው ምግባቸውን እንደሚሰጣቸው፤ እንደዚሁም እግዚአብሔር ለሰው ልጅ ብቻ ሳይኾን በሰፊው እጁ (በማያልቅ ቸርነቱ) በሥርዓቱ ጸንተው ለሚኖሩ ለእንስሳት ጭምር ምግባቸውን እየሰጠ ደስ እንደሚያሰኛቸው የሚያስረዳ ኃይለ ቃል ነው፡፡

የቤተ ክርስቲያናችን መተርጕማን እንደሚያትቱት ከሰው ልጅ በቀር ከእግዚአብሔር ሥርዓት የወጣ እንስሳ የለም፤ ማለትም ሰው እንጂ እንስሳት ሕገ እግዚአብሔርን አልተላለፉም፡፡ ነገር ግን የሰው ልጅ አምላክነትን ተመኝቶ ‹‹አትብላ›› የተባለውን ዕፅ በመብላት ሕጉን፣ ትእዛዙን ተላልፏል፡፡ እግዚአብሔርም ይቅር ባይ አምላክ ነውና የሰውን ልጅ (የአዳምን) ንስሐ ተመልክቶ፣ ኀጢአቱን ይቅር ብሎ ሞቱን በሞቱ ሽሮ አድኖታል፡፡ እግዚአብሔር አምላችን በፍጡራኑ የማይጨክን፤ የለመኑትን የማይነሳ፤ የነገሩትንም የማይረሳ አምላክ መኾኑን በማስተዋልና ቸርነቱን ተስፋ በማድረግ በምድር በረከቱን እንዲሰጠን፤ ቅዱስ ሥጋውን ለመብላት፣ ክቡር ደሙን ለመጠጣ እንዲያበቃን፤ በሰማይም ዘለዓለማዊ መንግሥቱን እንዲያወርሰን እኛም በንጹሕ ልብ ኾነን ዘወትር ልንማጸነው ይገባናል፡፡ በሰው ከመታመን ይልቅ በእግዚአብሔር መታመን ይበልጣልና (መዝ. ፻፲፯፥፰)፡፡ ደግሞም ‹‹አንተን ተስፋ የሚያደርጉ አያፍሩም›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (መዝ. ፳፬፥፫) እግዚአብሔርን ተስፋ ማድረግ አያሳፍርምና፡፡

ይቆየን

ዘመነ ክረምት – ክፍል አራት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! በክፍል ሦስት ዝግጅታችን ከሐምሌ ፲፱ እስከ ነሐሴ ፱ ቀን ድረስ ያለው ሁለተኛው ክፍለ ክረምት መብረቅ፣ ነጐድጓድ፣ ባሕር፣ አፍላግ፣ ጠል እንደሚባል በማስታወስ ከወቅቱ ጋር ተያያዥነት ያለው ትምህርት አቅርበን ነበር፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን ደግሞ ቀጣዩን ክፍል ይዘን ቀርበናል፡፡ መልካም ንባብ!

፫. ዕጕለ ቋዓት፣ ደሰያት፣ ዓይነ ኲሉ

ከነሐሴ ፲ እስከ ፳፯ ቀን (ከማኅበር እስከ አብርሃም) ድረስ ያለው ሦስተኛው የዘመነ ክረምት ክፍለ ጊዜ (ንዑስ ክፍል) ‹ዕጕለ ቋዓት፣ ደሰያት፣ ዓይነ ኲሉ› ይባላል፡፡ ይኸውም የሰው ልጅ ብቻ ሳይኾን የሰማይ አዕዋፍ፣ የምድር አራዊትና እንስሳት ሳይቀሩ እግዚአብሔርን አምነው በተስፋ መኖራቸው የሚዘከርበት፤ በተጨማሪም በዝናም አማካይነት በዙርያቸው ያለው የውኃ መጠን ከፍ ሲልላቸው ደሴቶች ዅሉ በልምላሜ ማሸብረቃቸው የሚነገርበት ክፍለ ክረምት ነው፡፡ በዚህ ወቅት በቤተ ክርስቲያን የሚነገረው ቃለ እግዚአብሔር ዅሉ በእነዚህ ምሥጢራት ላይ ያተኮረ ነው፡፡ ከዚህ ቀጥለን ስለ ዕጕለ ቋዓት፣ ደሰያትና ዓይነ ኲሉ በቅደም ተከተል ማብራሪያ ለመስጠት እንሞክራለን፤

ዕጕለ ቋዓት

‹ዕጕል፣ ዕጓል› ማለት ‹ልጅ›፤ ‹ቋዕ› ደግሞ ‹ቍራ› ማለት ነው፡፡ ‹ቋዕ› የሚለው ቃል በብዙ ቍጥር ሲገለጽም ‹ቋዓት› ይኾናል፡፡ በዚህ መሠረት ‹ዕጕለ ቋዓት› የሚለው የግእዝ ቃላት ጥምረትም (ሐረግ) ‹የቍራ ልጆች (ግልገሎች፣ ጫጩቶች)› የሚል ትርጕም አለው፡፡ በዚህ ወቅት በቤተ ክርስቲያን የቍራ ጫጩቶች አስተዳደግ ከምእመናን ሕይወት ጋር ተነጻጽሮ ይነገራል፡፡ ይህም እንዲህ ነው፤ የቍራ ጫጩት ከእንቍላሉ ፍሕም መስሎ ይወጣል፡፡ በዚህ ጊዜ እናትና አባቱ ባዕድ ነገር የተወለደ መስሏቸው ትተውት ይሸሻሉ፡፡ እርሱም በራበው ጊዜ ምግብ ፍለጋ አፉን ይከፍታል፡፡ በዚህ ሰዓት ርጥበት የሚፈልጉ ተሐዋስያን ወደ አፉ ይገባሉ፡፡ ከዚያም አፉን በመግጠም ይመገባቸዋል፡፡ እንደዚሁም ተሐዋስያን በአጠገቡ ሲያልፉ በእስትንፋሱ (በትንፋሹ) እየሳበ ይመገባቸዋል፡፡ የቍራ ጫጩት እስከ ፵ ቀን ድረስ እንደዚህ እያደረገ ከቆየ በኋላ ቀስ በቀስ ፀጕር ያበቅላል፤ ከዚህ በኋላ በመልክ እነርሱን እየመሰለ ስለሚመጣ እናት አባቱ ተመልሰው ይከባከቡታል፡፡ ይህ የቍራ ዕድገትና ለውጥም እግዚአብሔር ፍጡራኑን የማይረሳ አምላክ እንደ ኾነ፣ ፍጥረቱንም በጥበቡ እየመገበ እንደሚያኖራቸው ያስገነዝበናል፡፡

ቅዱስ ዳዊት ይህን የቍራ የዕድገት ደረጃና የእግዚአብሔርን መግቦት በተናገረበት መዝሙሩ ‹‹ወሐመልማለ ለቅኔ ዕጓለ እመሕያው ዘይሁቦሙ ሲሳዮሙ ለእንስሳ ወለዕጕለ ቋዓት እለ ይጼውዕዎ፤ ለሰው ልጆች ጥቅም ለምለሙን የሚያበቅል፤ ለእንስሳትና ለሚለምኑት የቍራ ጫጩቶች ምግባቸውን የሚሰጣቸው እርሱ ነው›› ሲል ይዘምራል (መዝ. ፻፵፮፥፱)፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በትርጓሜያቸው እንደ ገለጹት ይህ ኃይለ ቃል እግዚአብሔር አምላክ ለእርሱ ለሚገዙ የሰው ልጆች እኽሉን፣ ተክሉን የሚያበቅልላቸው፤ ለእንስሳቱና ለአዕዋፍ ምግባቸውን የሚሰጣቸው እርሱ እንደ ኾነ ያስረዳል፡፡ ‹‹… ወለዕጕለ ቋዓት እለ ይጼውዕዎ፤ … ለሚለምኑት ለቍራ ጫጩቶች›› የሚለው ሐረግም አዕዋፍ፣ ምግብ እንዲያዘጋጅላቸው እግዚአብሔርን እንደሚለምኑትና እርሱም ልመናቸውን እንደሚቀበላቸው ያስገነዝበናል፡፡ በመዝሙረ ዳዊት አንድምታ ትርጓሜ እንደ ተጠቀሰው ‹‹ወለዕጕለ ቋዓት እለ ይጼውዕዎ›› የሚለው ሐረግ ‹‹… እለ ኢይጼውዕዎ›› ተብሎ ሊነገር ይችላል፤ ይህም የቍራ ጫጩቶች አፍ አውጥተው ባይነግሩትም እንኳን እርሱ ፍላጎታቸውን ዐውቆ የዕለት ምግባቸውን እንደሚያዘጋጅላቸው የሚያመለክት ምሥጢር አለው፡፡ ምሥጢሩን ወደ እኛ ሕይወት ስናመጣውም እግዚአብሔር አምላክ ስሙን የሚጠሩትንም የማይጠሩትንም፤ ‹‹የዕለት እንጀራችንን ስጠን›› እያሉ የሚማጸኑትንም የማይጸልዩትንም በዝናም አብቅሎ፣ በፀሐይ አብስሎ ሳያደላ ዅሉንም በቸርነቱ እንደሚመግባቸው ያስተምረናል፡፡ ‹‹… እርሱ ለክፎዎችና ለደጎች ፀሐይን ያወጣልና፤ ለጻድቃንና ለኃጥአንም ዝናምን ያዘንማልና፤›› እንዳለ ጌታችን በወንጌል (ማቴ. ፭፥፵፭)፡፡

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ቍራዎችንና የሌሎችንም አዕዋፍ አኗኗር ምሳሌ በማድረግ ስለ ምድራዊ ኑሮ ሳይጨነቁ እግዚአብሔርን ተስፋ በማድረግ መኖር እንደሚገባን በቅዱስ ወንጌል አስተምሮናል፡፡ እንዲህ ሲል፤ ‹‹ለነፍሳችሁ በምትበሉት ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፡፡ ነፍስ ከመብል ሰውነትም ከልብስ ይበልጣልና፡፡ ቍራዎችን ተመልከቱ፤ አይዘሩም፤ አያጭዱምም፡፡ ዕቃ ቤትም ወይም ጎተራ የላቸውም፤ እግዚአብሔርም ይመግባቸዋል፡፡ እናንተ ከወፎች ትበልጡ የለምን? … አበቦችን እንዴት እንዲያድጉ ተመልከቱ፤ አይደክሙም፤ አይፈትሉምም … ዛሬ ያለውን፣ ነገም ወደ እቶን የሚጣለውን በሜዳ የኾነውን ሣር እንዲህ የሚያለብሰው ከኾነ፣ እናንተ እምነት የጐደላችሁ! እናንተንማ ይልቁን እንዴት? … የምትበሉትን የምትጠጡትንም አትፈልጉ፤ አታወላውሉም፡፡ ይህንስ ዅሉ በዓለም ያሉ አሕዛብ ይፈልጉታልና፡፡ የእናንተም አባት ይህ እንዲያስፈልጋችሁ ያውቃል፡፡ ዳሩ ግን መንግሥቱን ፈልጉ፤ ይህም ዅሉ ይጨመርላችኋል፤›› (ሉቃ. ፲፪፥፳፪-፴፩)፡፡

ከዚህ ላይ ‹‹… ለነፍሳችሁ በምትበሉት ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ …›› የሚለው ኃይለ ቃል እንደ እንስሳት ሳትሠሩ እግዚአብሔር ምግብ እንዲሰጣችሁ ለምኑት ማለት እንዳልኾነ ማስተዋል ተገቢ ነው፡፡ ኃይለ ቃሉን ለማብራራት ያህል የሰው ልጆች ከእንስሳት ከምንለይባቸው ባሕርያት አንደኛው ሠርተን መብላት መቻላችን ነው፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትም የታታሪነትንና የሠርቶ ማደርን ጥቅም እንጂ ሳይሠሩ ተቀምጦ መብላትን አላስተማሩንም፡፡ በብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች የሰው ልጅ እጁ ከሥራ መለየት እንደማይገባው ተገልጿል፡፡ ለምሳሌ አባታችን አዳም ከሳተ በኋላ በምድር ጥሮ፣ ግሮ እንዲኖር ተፈርዶበታል፡፡ ይህንም ‹‹… የምድርንም ቡቃያ ትበላለህ፡፡ ወደ ወጣህበት መሬት እስክትመለስ ድረስ በፊትህ ወዝ እንጀራን ትበላለህ›› ከሚለው ኃይለ ቃል ለመረዳት እንችላለን (ዘፍ. ፫፥፲፰-፲፱)፡፡ በተመሳሳይ መልኩ እግዚአብሔር አማላክ አዳምን ከዔደን ገነት ያስወጣው የተገኘባትን መሬት ያርስ ዘንድ መኾኑም ተጠቅሷል (ዘፍ. ፫፥፳፫)፡፡ ይኸውም የሰው ልጅ ሠራቶ አዳሪ ፍጥረት መኾኑን የሚያመላክት ምሥጢር ነው፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞንም ‹‹አንተ ታካች! እስከ መቼ ትተኛለህ? ከእንቅልፍህስ መቼ ትነሣለህ? ጥቂት ትተኛለህ፤ ጥቂት ታንቀላፋለህ፡፡ ትተኛም ዘንድ ጥቂት እጅህን ታጥፋለህ፡፡ እንግዲህ ድህነትህ እንደ ወንበዴ፣ ችጋርህም ሰይፍ እንደ ታጠቀ ሰው ይመጣብሃል›› በማለት የሰው ልጅ እንቅልፍን (ስንፍናን) ካበዛና ካልሠራ ክፉ ድህነት እንደሚመጣበት ተናግሯል (ምሳ. ፮፥፱-፲)፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ ‹‹ከእናንተ ሊሠራ የማይወድ አይብላ›› በማለት ሥራ የማይወድ ሰው ምግብ መሻት እንደሌለበት አስረድቷል (፪ኛ ተሰ. ፫፥፲)፡፡

መጽሐፍ ቅዱስ ስንፍናን የሚያወግዝ፣ ሥራን ደግሞ የሚያበረታታ ኾኖ ሳለ ‹‹ለምንድን ነው መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹ለነፍሳችሁ በምትበሉት ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ …› ሲል ያስተማረው?›› የሚል ጥያቄ ሊነሣ ይችላል፡፡ ለጥያቄው ምላሽ ለመስጠት ያህል ቃሉ አትጨነቁ ማለቱ ‹‹ለሥጋዊ ጉዳይ ቅድሚያ አትስጡ፤ እየሠራችሁ እግዚአብሔርን በጸሎት ጠይቁ›› ሲለን ነው፡፡ የሰው ልጅ ሠራተኛ ፍጥረት ቢኾንም ዝናም አልጥልለት ሲል፤ የዘራበት መሬት ሳያበቅል ሲቀር፤ የወር ደመወዙ ሲዘገይ፤ እኽል የሚሸምትበት ገንዘብ ሲያጣ፤ ወዘተ. በመሳሰሉት ፈተናዎች ውስጥ በኾነ ጊዜ ምን ልበላ ነው? ልጠጣ ነው? ልጆቼ እንዴት ሊኾኑብኝ ነው? ዛሬን እንዴት ላልፍ ነው? በሚሉትና በመሳሰሉት የጭንቀትና የተስፋ መቍረጥ ስሜቶች ሳይያዝ የዕለት ጕርሱን፣ የዓመት ልብሱን ይሰጠው ዘንድ የጠፋውን ዝናም ማምጣት፤ የደረቀውን ዘር ማለምለም፤ ባዶ የኾነውን ቤት መሙላት የሚቻለውን እግዚአብሔርን (እርሱን) በእምነት ኾኖ በጸሎት ይጠይቀው ለማለት መድኀኒታችን ክርስቶስ ‹‹ለነፍሳችሁ በምትበሉት ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ›› ብሎናል፡፡ ሐሳቡ ሲጠቃለል የሰው ልጅ ይርበኛል፣ ይጠማኛል ማለቱን ትቶ በእግዚአብሔር አምሳል መፈጠሩን በማሰብ ዓቅሙ በሚችለው ዅሉ እንዲሠራ፤ የጐደለውን እንዲሞላለት ደግሞ ጸሎቱን ወደ ፈጣሪው እንዲያቀርብ ሲያስረዳ ጌታችን ‹‹ለነፍሳችሁ በምትበሉት፣ ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ›› በማለት አስተምሯል፡፡

ይህም የሰው ልጅ ለሚበላው፣ ለሚጠጣው መጨነቅ እንደማይገባውና እየሠራ ሙሉ ተስፋውን በእግዚአብሔር ላይ ማድረግ እንዳለበት፤ ከዅሉም በላይ ለምድራዊው ኑሮው ድሎት ሳይኾን ሰማያዊውን መንግሥት ለመውረስ መትጋት እንደሚጠበቅበት ያስገነዝባል፡፡ ስለዚህም አምላካችን እንዳስተማረን ስለምንበላውና ስለምንጠጣው ሳይኾን ስለ በጎ ምግባርና ስለ ዘለዓለማዊው መንግሥት መጨነቅ ይገባናል ማለት ነው፡፡ ራሳችንን ለመንግሥተ እግዚአብሔር በሚያበቃ የጽድቅ ሥራ ካስገዛን ለሥጋችን የሚያስፈልገን ምድራዊ ዋጋም አብሮ ይሰጠናልና፡፡ ‹‹ወዘእንበለ ንስአሎ ይሁብ ፍትወተነ ዘእምፈቃዱ፤ ሳንለምነው ልባችን የተመኘውን በፈቃዱ የሚሰጠን እርሱ ነው›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (መጽሐፈ ኪዳን)፡፡ ‹‹ይሰጠዎ ወይሰምዖ ጸሎቶ ለኵሉ ለዘሰአሎ እግዚአ ለሰንበት አምላከ ምሕረት ያርኁ ክረምተ በበዓመት ይሰምዑ ቃሎ ደመናት፤›› በማለት ቅዱስ ያሬድ በዘመነ ክረምት መዝሙሩ ያቀረበው ምስጋናም ይህንኑ እውነት የሚያንጸባርቅ ኃይለ ቃል ነው፡፡ ትርጕሙም፡- ‹‹እግዚአብሔር አምላክ የለመነዉን ፍጥረት ዅሉ ጸሎት ተቀብሎ ምላሽ ይሰጣል፡፡ የሰንበት (የፍጥረታት) ጌታ እርሱ የምሕረት (የይቅርታ) አምላክ ነው፡፡ የምሕረት አምላክ በመኾኑም በየዓመቱ (በየጊዜው፣ በየዘመኑ) ወርኃ ክረምትን (ወቅቶችን) ያፈራርቃል፡፡ ደመናትም (ፍጥረታትም) ቃሉን ይሰማሉ (ትእዛዙን ይፈጽማሉ)፤›› ማለት ነው፡፡

ይቆየን