ታላቅ የቪሲዲ ምርቃት
አዘጋጅ፡- በኢ/ኦ/ተ/ቤተ ክርስቲያን ሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ሙያ አገልግሎትና አቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል
ቦታ፡-ጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ
ሰዓት፡- ቅዳሜ ኅዳር 02/03/2004 ዓ.ም ከቀኑ 7፡30 ጀምሮ
አዘጋጅ፡- በኢ/ኦ/ተ/ቤተ ክርስቲያን ሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ሙያ አገልግሎትና አቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል
ቦታ፡-ጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ
ሰዓት፡- ቅዳሜ ኅዳር 02/03/2004 ዓ.ም ከቀኑ 7፡30 ጀምሮ
{gallery count=1 width=350 height=300 counter=1 links=0 alignment=center animation=3000}smg30{/gallery}
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን 30ኛው መደበኛ መንፈሳዊ ጉባኤ ጥቅምት 7 ቀን 2004 ዓ.ም በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ከጠዋቱ 3 ሰዓት በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ጸሎተ ቡራኬ ተጀምሯል፡፡
የ48ቱ አህጉረ ስብከት ሊቃነ ጳጳሳት በከፊል የተገኙ ሲሆን ሁሉም የሀገር ውስጥ ሥራ አስኪያጆች ፣የመንበረ ፓትሪያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ሓላፊዎች ፣በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር የሚገኙ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች ፣ በኢትዮጵያ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ፣ የሕፃናትና ቤተሰብ ጉዳይ ድርጅት፣ የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ሓላፊዎች የጉባኤው ተሳታፊዎች ናቸው።
ቅዱስነታቸው በጸሎተ ወንጌል ጉባኤውን ባርከው ከከፈቱ በኋላ በሰጡት ቃለ ምእዳን ሰው መግባባት የሚችለው እግዚአብሔር በሰጠው አእምሮ ሲጠቀምበትና በፈሪሃ እግዚአብሔር ሲኖር ነው። ፈሪሃ እግዚአብሔር ካለ ሰላም፣ ፍቅር፣ መግባባት፣ መዋደድና መከባበር ይኖራል ብለው በሰላማዊ መንገድ ሓላፊነትን መወጣት እንዲገባ አሳስበዋል፡፡
ቅዱስ ፓትርያርኩ አያይዘው በ2003 ዓ.ም በሞት የተለዩንን ብፁዕ አቡነ በርናባስን፣ ብፁዕ አቡነ ይስሐቅንና ብፁዕ አቡነ ሚካኤልን በጸሎት እናስባቸው ብለው ጸሎት አድርሰዋል፡፡
ሊቀትጉሃን ኃይለ ጊዮርጊስ ዳኜ፣ መጋቤ ሰናያት አሰፋ ስዩም፣ ሊቀ ስዩማን ራደ አስረስ፣ ንቡረ እድ ተስፋዬ ተወልደና መጋቤ ሐዲስ ይልማ ቸርነት የአቋም መግለጫ ረቂቅ እንዲያዘጋጁ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ ለጉባኤው አቅርበው ጉባኤው የተመረጡትን አርቃቂዎች በሙሉ ድምጽ አሳልፈዋል፡፡
ከረፋዱ 4 ሰዓት ጀምሮ ለ45 ደቂቃ ያህል የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት አጠቃላይ ሪፓርት በብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የጠቅላይ ቤተ ክርህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የኢሉባቡርና ጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና በንቡረ እድ ኤልያስ አብርሃ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ ቀርቧል፡፡ ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሪፖርት ቀጥሎ የትግራይ ማዕከላዊ ዞን /አክሱም/ ሀገረ ስብከት ሪፖርት መቅረብ የነበረበት ቢሆንም የጋምቤላ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ለሌላ ተልእኮ ወደ ሱዳን ሀገረ ስብከት መሔድ እንዲችሉ ፈቃድ ጠይቀው ቅድሚያ ሪፖርታቸውን አቅርበዋል፡፡
በጠዋቱ መርሃ ግብር የትግራይ ማዕከላዊ ዞን፣ የሲዳማ፣ የሰሜን ጎንደር፣ የምሥራቅ ሀረርጌ፣ ሀገረ ስብከት ሪፖርት ቀርቧል፡፡ ከሰዓት በኋላ በተያዘው መርሃ ግብር ከቀኑ 8 ሰዓት እስከ 11፡30 ድረስ የጅማ ዞን ሀገረ ስብከት፣ በትግራይ ክልል ሀገረ ስብከት የመቀሌ፣ የኢሊባቡር፣ የድሬዳዋ፣ የጋሞጎፋ፣ የሰሜን ወሎ፣ የባሌ፣ የደቡብ ጎንደርና የምሥራቅ ወለጋ አህጉረ ስብከት ሪፖርት ቀርቧል፡፡
ረቡዕ ጥቅምት 8 ቀን 2004 ዓ.ም ከጠዋቱ 3 እስከ 6፡30 በነበረው መርሐ ግብር የአርሲ፣ የትግራይ ምሥራቅ /አዲግራት/፣ የምዕራብ ጎጀም፣ የከፋ ቦንጋ፣ የሰሜን ሸዋ፣ የአሶሳና የደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ሪፖርት ቀርቦ እንዳበቃ የቆሜ አቋቋም ሊቃውንት ወረብ አቅርበዋል፡፡
በሊቃውንቱ የቀረበው ወረብ እንደተጠናቀቀ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ፣ የምሥራቅ ጎጃም፣ የምዕራብ ሐረርጌና የትግራይ ደቡባዊ ዞን /ማይጨው/ አህጉረ ስብከት ሪፖርት በንባብ ተሰምቷል፡፡
ከሰዓት በኋላ በተያዘው መርሃ ግብር የደቡብ ኦሞ፣ የሰሜን ምዕራብ ሸዋ የሰላሌ ሀገረ ስብከት የሐዲያና ስልጤ፣ የዋግ ሕምራ፣ የምዕራብ ሸዋ፣ የአፋር፣ የአዊ ዞን፣ የሶማሊያ፣ የምዕራብ ወለጋ፣ የትግራይ ሰሜናዊ ምዕራብ ዞን ሽሬ ሀገረ ስብከትና የትግራይ ሰሜናዊ ምዕራብ ዞን ሽሬ ሀገረ ስብከትና የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሪፖርት ከቀረበ በኋላ ውይይት ተካሒዷል፡፡
30 ዓመት ያስቆጠረው የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ካሳለፈው ረዥም ጉዞ ጋር ሲነጻጸር የሚጠበቅበትን ውጤት እያስመዘገበ እንዳልሆነ በመንበረ ፖትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት የቀረበው ሪፓርት ያስረዳል፡፡
አጠቃላይ ጉባኤው እስከ ጥቅምት 11 ቀን 2004 ዓ.ም የሚቀጥል ሲሆን ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅሙ ውይይቶችና የውሳኔ ሐሳቦች እንደሚቀርቡበት ይጠበቃል፡፡
የኢትዮጵያን ዕሥራ ምዕት ምክንያት በማድረግ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስትያን ታሪክ ከልደተ ክርስቶስ እስከ 2000 ዓ.ም” በሚል ርእስ የተዘጋጀው መድበል ይህንኑ ሐሳብ ሲያጠናክር፤ “ቅዱስ አባ ሰላማ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ መንበረ ጵጵስናውን አክሱም ላይ አድርጎ በሀገራችን የወንጌልን ብርሃን በሰፊው ስለገለጠ ከሣቴ ብርሃን ተባለ” ይልና “በዚሁ በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በዓለም አቀፍ ደረጃ የታወቀች ብሔራዊት ቤተ ክርስቲያን ለመሆን መብቃቷን ታሪክ ያስረዳል” ይላል፡፡
ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም በመጣበት ወቅት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን መሥርቶአል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያቱን “እኔን ማን ትሉኛላችሁ?” ብሎ በጠየቃቸው ጊዜ “አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ” ብሎ ቅዱስ ጴጥሮስ መልሶ ነበር፡፡ ከዚህም በኋላ “አንተ ዓለት ነህ በዚህችም ዓለት ላይ ቤተ ክርስቲያኔን እሠራታለሁ፤ የሲኦልም ደጆች ሊያናውጿት አይችሉም፡፡” በማለት ቤተ ክርስቲያንን በሐዋርያት መሠረት ላይ መሠረተ/ማቴ.16÷16-18/፡፡
ይህ ሐዋርያ በመልእክታቱ ምእመናንን ሲገሥጽና ሲመክር ሲያስተምር የኖረ ሲሆን በሁለተኛይቱ መልእክቱ ላይ ግን ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆነ ኃይለ ቃልን ጽፏል፡፡ “ስለዚህ እነዚህን ነገሮች ምንም ብታውቁ በእናንተም ዘንድ ባለ እውነት ብትጸኑ ስለ እነዚህ ዘወትር እንዳሳስባችሁ ቸል አልልም፡፡ ሁል ጊዜም በዚህ ማደሪያ ሳለሁ በማሳሰቤ ላነቃችሁ የሚገባኝ ይመስለኛል፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳመለከተኝ ከዚህ ማደሪያዬ መለየቴ ፈጥኖ እንዲሆን አውቃለሁና፡፡ ከመውጣቴም በኋላ እነዚህን ነገሮች እንድታስቡ በየጊዜው ትችሉ ዘንድ እተጋለሁ” /2ኛጴጥ. 1÷13-15/
ብታውቁም፤ ብተጸኑም ማሳሰቤን ቸል አልልም!
ቅዱስ ጴጥሮስ በመልእክታቱ ስለ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነትና ስለ ሰው ልጅ ብሎ ስለተቀበለው መከራ፣ ክርስቲያኖች ሊኖራቸው ስለሚገባ መንፈሳዊ አኗኗር፣ አለባበስ፣ ስለ ጋብቻና ቤተሰባዊ ጉዳዮች፣ በምእመናን ላይ ስለሚመጡ መከራዎችና የዲያብሎስ ውጊያዎች፣ ድል ሲያደርጉም ስለሚያገኙት ጸጋና ዋጋ፣ ስለሚደርሱበት መዓርግ በአጠቃላይ በቀላሉ ተዘርዝሮ የማያልቅ ሰፊ ትምህርትን በመልእክቱ አስተምሯል፡፡ ይሁንና ሐዋርያው አውቀውታል፣ ጸንተዋል ብሎ ማሳሰቡን አላቆመም፡፡ ሰው ከመንገድ የሚስተው በእውቀት ጉድለት ብቻ አይደለም፡፡ እያወቁ መሳት፣ ጸናሁ ሲሉም መጥፋት አለ፡፡ ስለዚህም “አሳስባችሁ ዘንድ ቸል አልልም፡፡” አለ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ መንጋውን ጠብቅና አሰማራ የተባውን አደራ የማይረሳ፣ በጥበቃ ተሰላችቶ ቸል የማይል፣ ትናንት የበሉት የጠጡት ይበቃቸዋል የማይል በመሆኑ ያውቁታል ብሎ ከመናገር ሳይቆጠብ “ዘወትር እንዳሳስባችሁ ቸል አልልም፡፡” አለ፡፡
በዚህ ማደሪያ ሳለሁ!
ሥጋ የነፍስ ማደሪያ ናት፤ አዳሪዋ ነፍስ ከማደሪያዋ ሥጋ ስተለይ ሰው ያን ጊዜ ሞተ ይባላል፡፡ “ከነፍስ የተለየ ሥጋ የሞተ ነው” እንዲል /ያዕ.2÷26/ ጻድቁ ኢዮብም “ይህ ቁርበቴም ከጠፋ በኋላ÷ በዚያን ጊዜ ከሥጋዬ ተለይቼ እግዚአብሔርን እንዳይ አውቃለሁ፡፡” ኢዮ.19÷26/ ያለው ሥጋ ጊዜያዊ ማደሪያ መሆኑን ሲያስረዳና ራሱን ከነፍስ አንጻር አድርጎ በሞት ሥጋውን ጥሎ እንደሚሄድ ሲናገር ነበር፡፡
ቅዱስ ጴጥሮስ “በዚህ ማደሪያዬ ሳለሁ በማሳሰቤ ላነቃችሁ ይገባኛል፡፡” ሲል በሥጋዬ ሳለሁ፣ ነፍሴ ሳትወሰድ ማለቱ ነበር፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስን ቀሪ ዕድሜውን በችኮላ የሚጠቀመው ለሌላ ሥጋዊ ተርታ ጉዳዮች ሳይሆን ምእመናን ያስተማረውን ትምህርት እንዳይገድፍና አንዳይጠፉበት በማሳሰብ ማንቃት ነው፡፡
ጌታዬ እንዳመለከተኝ መለየቴ ፈጥኖ እንዲሆን አውቃለሁ!
“በእግዚአብሔር ፊት የቅዱሳኑ ሞት የከበረ” ስለሆነ ሞት ለቅዱሳን ድንገተኛና ያልተጠበቀ አይሆንባቸውም፡፡ እርግጥ ነው ሰው ሁሉ ሟች እንደ ሆኑና የሞትን አይቀሬነት በመጥቀስ ሁሉም ሰው እንደሚሞት ያውቃል ሊባል ይችላል፡፡ ቅዱሳን ግን የሚሞቱ መሆናቸውን የሚያውቁት ሞት አይቀርም ብለው ሳይሆን የሚሞቱበትን ጊዜና ሁኔታ ለመረጣቸው ለባሪያዎቹ የሚያደርገውን የማይሠውር እግዚአብሔር ገልጣላቸው ነው፡፡ የሚከተሉት የሊቀ ነቢያት ሙሴንና የቅዱስ ጳውሎስን ንግግሮች እንመልከት፡-
“እኔ ግን በዚህች ምድር እሞታለሁ ዮርዳኖስንም አልሻገርም” /ዘዳ.4÷22/
“በመሥዋዕት እንደሚደረግ የእኔ ሕይወት ይሠዋልና የምሄድበትም ጊዜ ደርሷል” /2ኛጢሞ.4÷6/
እነዚህ ታላላቅ ቅዱሳን የሚሞቱ መሆናቸቸውን ብቻ ሳይሆን የሚሞቱበትን ቦታ ጊዜ አስቀድመው መናገራቸው ከእግዚአብሔር ስለተነገራቸው ነው፡፡ የቅዱሳን አባቶቻችንን እና የቅዱሳት እናቶቻችንን ገድላት ስንመረምር ቅዱሳን ዕለተ እረፍታቸው ቀድሞ በእግዚአብሔር እንደሚነገራቸው እንረዳለን፡፡
ቅዱስ ጴጥሮስም ሰው እንደመሆኑ “መሬት ነህና ወደ መሬት ትመለሳለህ” ብሎ ጌታ ለሁሉ ካመለከተው ጥሪ በተጨማሪ ከቅዱሳን አንዱ እንደመሆኑ ከመሞቱ በፊት እንደሚሞት ያውቅ ነበር፡፡ ጌታችን ከዕርገቱ በፊትና ከዕርገቱ በኋላ ሁለት ጊዜ ተገልጦ ስለሞቱ ነግሮታል፡፡
ከዕርገቱ በፊት ከላይ የጠቀስነውን የእረኝነት አደራ ከሰጠው በኋላ “እውነት እውነት እልሃለሁ አንተ ጎልማሳ ሳለህ ወገብህን በገዛ ራስህ ታጥቀህ ወደምትወደው ትሄድ ነበር፤ ነገር ግን በሸመገልህ ጊዜ እጆችህን ትዘረጋለህ ሌላውም ያስታጥቅሃል ወደማትወደውም ይወስድሃል፡፡” ብሎታል፡፡ ወንጌልን ጽፎ በብዙ ቦታዎች የጻፈውን ሲተረጉምና ሲያትት የምናገኘው ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ ትርጓሜን ሳንሻ ንባቡ ላይ “በምን ዓይነት ሞት እግዚአብሔርን ያከብር ዘንድ እንዳለው ሲያመለክት ይህን አለ፡፡” ብሎ የጌታን ንግግር ትርጓሜ አስከትሎ ጽፎልናል፡፡
በእርግጥም ቅዱስ ጴጥሮስ በሸመገለ ጊዜ እጆቹን በተዘቀዘቀ መስቀል ላይ ዘርግቶ ቁልቁል መሰቀል ትንቢተ ክርስቶስን ፈጽሟል፡፡
ጌታችን ከዐረገ በኋላ ደግሞ ቅዱስ ጴጥሮስ በሮም ሲያስተምር “ልበ ንጹሖች ብጹዓን ናቸው፡፡” ብሎ ባስተማረው ትምህርት ሚስቶቻችንን አሸፈተብን ያሉ ሰዎች ተነሡበት፡፡ በዚህን ወቅት ሴቶቹ ተማክረው ቅዱስ ጴጥሮስ እንዲሸሽ ነገሩት ከከተማይቱ ወጥቶ ሊሄድ ሲል ጌታችን ተገልጦ ታየው “ጌታ ሆይ ወዴት ትሄደለህ” ቢለው “ዳግም በሮም ልሰቀል” በማለት ነገረው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ በዚህ ልቡ ተነክቶ ወደ ሮም ተመለሰና የሰማዕትነትን አክሊል ተቀዳጀ፡፡ “ጌታችን እንዳመለከተኝ” ያለው ይህን ነበር፡፡
ከመውጣቴም በኋላ አንድታስቡ በየጊዜው ትችሉ ዘንድ እተጋለሁ!
ከላይ የተመለከትናቸው ሃሳቦች ቅዱስ ጴጥሮስ ጊዜ ሞቱ እንደቀረበ አውቆ መናገሩን እና ምእመናን የተማሩትን በማሳሰብ ሲያነቃቸው እንደነበር የሚያስረዱ ናቸው፡፡ እስካሁን የተመለከትናቸው የሚያወሱት ይህ ሐዋርያት በሕይወት ሳለ ስለሚያደርጋቸው ነገር ነበር፡፡ በመጨረሻው ዐረፍተ ነገር ግን “ከመውጣቴ በኋላ የሚል ሐረግ እናገኛለን፡፡ “ከመውጣቴ በኋላ” ሲል ምን ማለቱ ነው?
ቀደም ባሉት ዐረፍተ ነገሮች እንደሚሞትና ይህንንም ጌታችን እንዳመለከተው ተናግሮ ነበር፡፡ ስለዚህ መውጣቴ ያለው ሞቱን እንደ ሆነ እሙን ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ሞት መውጣት ተብሎ ሲነገር የቅዱስ ጴጥሮስ የመጀመሪያ አይደለም፡፡ በታቦር ተራራ ከሙሴና ኤልያስ ጋር ስለመነጋገሩ በተጻፈበት ስፍራ “በክብርም ታይተው በኢየሩሳሌም ሊፈጽም ስላለው ስለ መውጣቱ ይናገሩ ነበር” ይላል፡፡ በኢየሩሳሌም የተፈጸመው መውጣቱ ደግሞ ሞቱ ነው፡፡ /ሉቃ.9÷31/ ስለዚህ ቅዱስ ጴጥሮስ ባስተማርኳችሁ እንድትጸኑ “ከሞትኩም በኋላ እተጋለሁ!” እያለ ነው፡፡ “ከሞትኩ በኋላ” የሚለውን እናቆየውና “እተጋለሁ!” የሚለውን ቃል በጥቂቱ እናብራራው፡፡
ትጋት ምንድርን ነው? ትጋት አንድ ነገር ያለማቋረጥ፣ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ፣ ያለመታከት ማድረግ ነው፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን “ታካች ሰው ምንም አደን አያድንም፤ የሰው የከበረ ሀብቱ ትጋት ነው” በማለት ትጋት የታካችነት ተቃራኒ መሆኑንና ጥቅሙን ተናግሯል /ምሳ.12÷27/፡፡ ጌታችን በምሴተ ሐሙስ ቅዱሳን ሐዋርያቱን “ከእኔ ጋር አንዲት ሰዓት እንኳን ልትተጉ አልቻላችሁምን? ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዩ” ብሎ ገሥጿቸው ነበር /ማቴ.26÷30/፡፡ ጸጋ መንፈስ ቅዱስን ከተቀበሉ በኋላ ግን ሐዋርያት ትጉሐን ነበሩ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ እንደ መሰከረላቸው “ወደዚህም ወደ ተሰፋ ቃል አሥራ ሁለቱ ወገኖቻችን ሌሊትና ቀን በትጋት እያመለኩ ይደርሱ ዘንድ አለኝታ አላቸው” /ሐዋ.26÷7/ በዚህ ሁሉ ትጋት አለመታከት፣ አንድን ነገር ሌሊትና ቀን ማድረግ መሆኑን ተረዳን፡፡
ቅዱስ ጴጥሮስ “ከመውጣቴም በኋላ እነዚህን ነገሮች እንድታስቡ በየጊዜው ትችሉ ዘንድ እተጋለሁ” ሲል የሚተጋው በምንድርን ነው? እየዞረ በማስተማር ይሆን? ይህማ ቢሆን ከመሄዴ በፊት ላሳስባችሁ ባላለን ነበር፡፡ ደግሞም ማስተማሩን በሚገባ ፈጽሞ በሰማዕትነት አርፏል፡፡ ታዲያ ከሞተ ወዲያ የሚተጋው ምን በማድረግ ነው? የትስ ነው የሚተጋው? መቼስ በመቃብር ያለሥጋው ሊተጋ አይችልም፡፡ “የሞቱትስ ተነሥተው ያመሰግኑሃልን? በመቃብርስ ውስጥ ቸርነትህን ይናገራሉን?” ብሏል ቅዱስ ዳዊት /መዝ.87÷15/ ራሱ ቅዱስ ጴጥሮስም “ከማደሪያዬ እለያለሁ፡፡ ብሎ ከሞተ ወዲያ እኔ የሚላት ነፍሱን እንደሆነ አስረድቶናል፡፡ ታዲያ በነፍሱ በሰማይ ምን እያደረገ ይሆን የሚተጋው? መቼስ በሰማይ እርሻ ቁፋሮ፣ ጽሕፈት፣ ድጒሰት የለም፡፡ ሐዋርያው በምን ይሆን የሚተጋው? በጸሎት ነዋ!
ስለዚህ ቅዱስ ጴጥሮስ “እንደተማራችሁት መኖርን እንዳትዘነጉ በየጊዜው /አንድ ጊዜ ብናስብ አንድ ጊዜ መዘንጋት አለና/ ትችሉ ዘንድ ከሞትኩም በኋላ ያለማቋረጥ ያለመሰልቸት ስለ እናንተ በመጸለይ እተጋለሁ! ማስተማርና መልእክትን ጽፎ መተው ብቻ ሳይሆን በተማራችሁት መገኘት እንድትችሉ በአጸደ ነፍስም ብሆን እለምናለሁ፣ እማልዳለሁ! እያለ ነው፡፡
በቅዱስ ጴጥሮስ ዓለትነት የተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በአደባባይ ስለእርሷ የተጻፋላት፣ በደሙ የዋጃት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሷ ነው፡፡ እርሱ በሁሉ የሞላ ሲሆን “ሁሉን በሁሉ ለሚሞላ ለእርሱ ሙላቱ የሆነች” አካሉ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት /ኤፌ.1÷22/፡፡ ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ አካሉ ስትሆን ክርስቶስ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ራሷ ነው፡፡ እኛ ደግሞ የሰውነት አካል ክፍሎች ነን፡፡ “እንግዲህ እናንተ የክርስቶስ አካሉ ናችሁ፤ እያንዳንዳችሁ የአካሉ ክፍሎች ናችሁ፡፡” ተብለናል /1ኛቆሮ.12÷27/፡፡ በቤተ ክርስቲያን ሕይወትን የሚሰጡ ጥምቀትን፣ ንስሐን፣ ቊርባንን የመሳሰሉ ምስጢራትን በመፈጸም ራሳችን ከሆነው ከመድኃኔዓለም ጋር አንድ እንሆናለን፡፡
ክርስቲያኖች ሲሞቱ ከዚህ ኅብረት ይነጠላሉ ማለት አይደለም፡፡ ራሷ ክርስቶስ በሰማይም በምድርም ስላለ ቤተ ክርስቲያንም በምድርም በሰማይም አለች፡፡ ስለዚህ አንድ ክርስቲያን ነፍሱ ከሥጋው ስትለይ ወደ ሰማያዊቱ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ይሄዳል፡፡ የሰማይዋ ቤተ ክርስቲያን ደግሞ ድል በነሱ ቅዱሳን የተሞላች ፍጹም መንፈሳዊ የሆነ ሥርዓት ያለባት፣ ሥጋዊ ደማዊ አሳብ የማይሰለጥንባት ናት፡፡ ከእኛ ተለይተው ወደዚያ ኅብረት የተደመሩ ወገኖቻችን በላይ ያሉ የክርስቶስ አካላት ናቸው፡፡ ከእኛ በምድር ካለነው የክርስቶስ አካላት ጋር አንድነታቸው አይቋረጥም፡፡ የክርስቶስ አካል አይከፈልማ! ስለዚህ በሰማይ ካሉት ድል የነሡ ቅዱሳን ጋር እኛ ደካሞቹ በጸሎት እንገናኛለን፡፡
“ዐይን እጅን አልፈልግሽም ልትላት አትችልም፤ ደካሞች የሚመስሉህ የአካል ክፍሎች ይልቁንም የሚያስፈልጉህ ናቸው፡፡ ተብሎ እንደተነገረ እኛ ኃጢአተኞቹ የቤተ ክርስቲያን የአካል ክፍሎች ብንሆንም ቅዱሳኑ ስለ እኛ ይጸልያሉ /1ቆሮ.12÷21/፡፡ ምክንያቱም ደካማ ብንሆንም ለቅዱሳን እናስፈልጋቸዋለን፡፡ ቅዱሳን ኃጥአንን ካልወደዱ ቅድስናቸውን ያጣሉ፡፡ እኛን ካልወደዱ “እኔ ክርስቶስን እንደመሰልሁ እናንተም እኔን ምሰሉ” “አሁን እኔ ሕያው ሆኜ አልኖርም፤ ክርስቶስ ግን በእኔ ይኖራል፡፡” ብለው ለመናገር እንደምን ይችላሉ? /ገላ.2÷20/
እኛ በሥጋ ድሆች የሆኑ ነዳያንን በመመጽወት እንደምንከብር ቅዱሳንም በነፍስ ድሆች የሆንን እኛን በአማላጅነት ጸሎታቸው እየመጸወቱ ይከብራሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ “ለድሀ ግን የሚራራ ምስጉን ነው፡፡” ይላልና በምግባር ድሆች ለሆንን ለእኛ መራራት የቅዱሳን ግብር ነው፡፡ “ጻድቅ ሰው ለእንስሳው ነፍስ ይራራል” ተብሎ እንደተነገረላቸው ቅዱሳን ክቡር ሆነን ሳለን ለማናውቅ እንደሚጠፉ እንስሶች ለመሰልን ለእኛ ለኃጢአተኞች ይራራሉ፤ ይማልዱማል /ምሳ.12÷10፣ 14÷21/፡፡
ቅዱሳን በሕይወተ ሥጋ እያሉ መከራን ታግሠው ስለ ሌሎች በደል ይለምናሉ፡፡ ሳይበድሉ ራሳቸውን በኃጢአትኛው ቦታ አርገው፣ ከደካሞች ጋር እንደ ደካማ ሆነው ይማልዳሉ፡፡ ታዲያ ነፍሳቸው ከሥጋቸው ተለይታ “ሲሄዱና ከክርስቶስ ጋር ሲኖሩ” /ፊል.1÷23/ ምንኛ ይለምኑ ይሆን?
በምድር ያለችው ቤተ ክርስቲያን በሕይወተ ሥጋ ለሌሉና ወደ ሰማዩ ኅብረት ለሄዱ ምእመናን ጸሎተ ፍትሐትን፣ መታሰቢያን በማድረግ፤ ለዚያ የሚያበቃ ቅድስና ያላቸውን ደግሞ በዓላቸውን በማክበር ታስባቸዋለች /2ጢሞ.1÷17-18/፡፡ በሰማይ ያሉት ቅዱሳን ደግሞ ቅዱስ ጴጥሮስ እንዳለው ስለ እኛ ይተጋሉ፡፡ የቤተ ክርስቲያንን መከራና የምእመናንን ስቃይም በዝምታ አይመለከቱም፡፡ በዙፋኑ ፊት ቆመው “ቅዱስና እውነተኛ ጌታ ሆይ እስከ መቼ ድረስ አትፈርድም? ስለ ደማችንስ በምድር በሚኖሩት ላይ እስከ መቼ አትበቀልም?” እያሉ ያማልዳሉ፡፡ /ራእ.6÷10/ የቅዱስ ጴጥሮስ በረከቱ አይለየን! አሜን፡፡
/ምንጭ፡ ሐመር ሐምሌ 2002 ዓ.ም./
ሚያዚያ 25፣ 2003ዓ.ም
ፕሮቴስታንቶችና ፕሮቴስታንታዊ መንገድ የሚከተሉ አንዳንዶች የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ወንጌልን አልሰበከችም የሚል ክርክር ይዘው ይቀርባሉ፡፡ ዝግጅት ክፍላችን ጥያቄያቸውን ለመመለስ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ምእመናንን በምላሹ እንዲሳተፉበት ጋብዘናል፡፡ ለዚህ እትም የያዝነውን እነሆ!
“ቤተክርስቲያናችን ዘመናትን የተሻገረችበት ኃይሏ ወንጌል ነው”
ቤተክርስቲያን ወንጌልን ስትሰብክ ሁለት ሺሕ ዓመታት አልፏታል። ይህንንም ሊቃውንቱ ምእመናንም ያስረዱትና የተረዱት ነው። ወንጌል ካልተሰበከ ክርስቲያኖች እንዴት ለአሁን ዘመን ደረሱ? ወንጌል መሠረት፣ በጎ እርሾ ሳይሆነው፣ ወንጌል ብርታት ሳይሆነው ይህን ሁሉ ዘመናት አቆራርጦ፣ ድልድዩን አልፎ እንዴት እዚህ ደረሰ? ወንጌል ቤተ ክርስቲያናችን ዘመናትን የተሻገረችበት ኃይሏ ነው፡፡
በቤተክርስቲያን ሊቃውንቱ የሚያነቧቸው፣ የሚተረጉሟቸው፣ ምእምናን የሚሰሟቸው፣ የሚታነጹባቸው ድርሳናት፣ ተአምራት ወንጌል ናቸው። እነዚህ መጻሕፍት ወንጌልን የሚፈቱ፣ የሚተረጉሙ፣ የሚያመሰጥሩ ናቸው። ከዚህ ውጭ የሆኑ መጻሕፍት በቤተክርስቲያን አይነበብም፣ አይተረጎምም፣ አይሰማም። ቤተክርስቲያን ወንጌልን የምትሰብከው በቃል፣ በመጽሐፍ ብቻ ሳይሆን በድርጊትም ነው። ጥምቀት ወንጌል ነው። ቤተክርስቲያንም ጥምቀት የዘወትር ሥራዋ ነው። ወንጌል ስለ ጥምቀት ነው የሚነግረን። የክርስቶስ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙም በየዕለቱ ይቀርባል፤ ይህ ወንጌል ነው። ወንድሞቻችን፣ እኅቶቻችን የተቀደሰውን ጋብቻቸውን በተቀደሰው ቦታ፣ በተቀደሰው ጸሎት በምስጢረ ተክሊል ይፈጽማሉ። ይህም ወንጌል ነው። እናቶቻችን፣ አባቶቻችን፣ ወንድሞቻችን፣ እኅቶቻችን ከዚህ ዓለም ሲሸኙ በሥርዐተ ፍትሐት፤ ብሉያትና ሐዲሳት እየተነበቡ፣ ያሬዳዊ ዜማ እየተዜመ ነው። ይህ ወንጌል ነው። አላዛርን ከመቃብር ተነሥ እንዳለው፤ የታሰረበትን ፍቱት እንደተባለ እንደተ ፈታ ሁሉ፤ ካህናትም ከኃጢአት እስራት እየፈቱ ሕዝባቸውን መሸኘት፤ “አቤቱ እግዚኦ ይቅር በለው ሲያውቅ፣ ሳያውቅ በሠራው ኃጢአት ይቅር በለው” እያሉ መሸኘት ወንጌል ነው።
ቤተክርስቲያን ራሷም፣ እግሯም፣ መሠረቷም፣ ጉልላቷም ወንጌል ነው። ይህን በቅንነት፣ በበጎ ነገር፣ በምስጢር፣ በትርጓሜ ለሚያዩት ነው። በጥላቻ ካዩት ነጩም ጥቁር ነው፤ ብርሃኑ ጨለማ ነው፤ በጥላቻ ማየትና በፍቅር ማየት፤ በሐሰት መናገርና በእውነት መናገር መካከል ሰፊ ልዩነት አለ። የቤተክርስቲያን ጥንተ ጠላቶች ለቤተክርስቲያን በጎ ይመሰክራሉ ብለን ከጠበቅን የተሳሳትን ይመስለኛል። መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸሐፍት ፈሪሳውያንን “እግዚአብሔር ከእናንተ ምስክርነትን አይፈልግም” ነው ያላቸው። ጸሐፍት ፈሪሳውያን ስለ ክርስቶስ በጎ ስለማይመሰክሩ ስለማይናገሩ ነው። ምክንያቱም በጭፍን፣ በቅናት፣ ስለጠሉት ነው። ቤተክርስቲያንም ከጠላቶቿ የእውነት ምስክርነትን አትጠብቅም፤ በበጎ ለሚያዩአት ግን ምስክርነቱ በእጅ የሚጨበጥ (የሚዳሰስ) በዐይነ የሚታይ ነው።ቤተክርስቲያን ወንጌል ያልሰበከችበት ዘመንም፣ ጊዜም የለም። ወንጌል አልተሰበከም ለሚሉ ሰዎች ትናንት አለነበሩም፣ ዛሬም የሉም። ለነገሩስ የት ሆነው ያዩታል? ቢኖሩም አይገባቸውም፤ ውስጣቸውም በብዙ ችግር የተተበተበ፤ በቅራኔ የተሞላ ነው። በቅራኔ የተሞላ ደግሞ ከውጭ የሚነገረውን በጎ ነገር ለመቀበል ዝግጁ አይደለም።
“ቤተክርስቲያን ክርስቶስን የምትሰብከው በቃል ብቻ ሳይሆን በድርጊትም ነው”
ሰው በተሰጠው የፈቃድ ነጻነት መሠረት የፈለገውን የመናገር መብት አለው። ፍሬ ነገሩ እውነቱ የቱ ነው? ሐሰቱስ? የሚ ለው ነው። ዲያብሎስ ስለ ቅዱስ ሚካኤል የብርሃን መላክነት አይመስክርም፤ ሊመሰክርም አይችልም። «ሚካኤል ደካማ ነው» እያለ የፈለገውን መናገር ይችላል። የዲያብሎስን ምስክርነትም ሚካኤል አይፈልገውም፣ አይቀበለውምም። ዲያበሎስ የፈለገውን ቢናገር ሚካኤልን አይከፋውም፤ ከጠላቱ ቡራኬ ስለማይጠብቅ። እንደዚሁ ሁሉ የእኛም ቤተክርስቲያን የሌሎችን ቤተእምነቶች ምስክርነትም ሆነ ክስ አታደንቀውም፤ አትደነግጥበትምም የእኛ ቤተክርስቲያን ጨርቅ ሰጥታ ጉቦ ሰጥታ እንዳልተስፋፋች ሁሉም ያውቁታል፤ ታዲያ ወንጌልና ክርስቶስን ሳትሰብክ ቤተክርስቲያን ሆና ሁለት ሺሕ ዓመታትን እንዴት ተሻገረች? አሸናፊ ስለሆነች በእውነቷ ብቻ ቆማ የምትኖር ናት። ጉቦ አይከፈልባትም፣ ማባበያም አትጠይቅም።
ቤተክርስቲያን ክርስቶስን የምትሰብከው በቃል ብቻ ልብን አሻክሮ ምላስን አለዝቦ በማነብነብ አይደለም፤ በድርጊት በማሳየትም እንጂ። በአንድ ታላቅ ዓመታዊ ክብረ በዓል በአንድ ቤተክርስቲያን በአንድ ቀን ብቻ የምናደርገው ስብሐተ እግዚአብሔር፤ ስብከቱ፣ ቅዳሴው፣ ማኅሌቱ፣ ዋዜማው በተግባርም ታቦት ይዘን ቆመን ያስተላለፍነው ትምህርት በጠቅላላው መናፈቃኑ ለአንድ ዓመት ከጮኹበት፣ ብዙ ነገር ካወጡበት «አገልግሎት» እጅግ ብልጫ አለው። የዚህ አጠቃላይ አገልግሎታችን ዋነኛ ማእከልም ወንጌልና የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነገረ ድኅነት ነው፡፡ ንዋያተ ቅድሳቶቻችን በሙሉ ስብከቶች ናቸው። በቅዳሴ ላይ ቄሱ፣ ዲያቆኑ መስቀል ይዞ የሚዞረው ምን ለማሳየት ነው? ቀሳውስት ዕጣን እያጠኑ “ስብሐት ወክብር ለሥሉስ ቅዱስ” እያሉ ሲያመሰግኑ ምስጢረ ሥላሴ እና ምስጢረ ሥጋዌን መስበከ፣ ማስተማራቸው ነው። ልብሰ ተክህኖዎቹ ከታቦተ ሕጉ ጀምሮ ንዋያተ ቅድሳቱ ሁሉ መስቀል የሚደረግበት ለጌጥ አይደለም። ይህ ስብከት አይደለም እንዴ? መቅደስ ውስጥ ስንቀድስ በአራቱ ማእዘን የምንቆመው ጽርሃ አርያምን እያሳየን ነው። እነርሱ የማያስተውሉትን ሰባቱ ሰማያትን አምጥተን መቅደሱ ላይ ቁጭ አድርገን የምናሳያቸው ለስብከት ነው። ኪሩቤል እንዴት አድርገው ጌታን እንደተሸከሙት ታቦቱን መንበሩ ላይ አስቀምጠን ስንቀደስ እናሳያለን። በተጨባጭ እያሳየን እያሰተማርን ነው።
ደስ ሊለን ይገባል፤ ለሁለት ሺሕ ዘመን ወንጌል ሳይነበብባት በተለያየም መንገድ ሳይሰበክባት የማትውል የማታድር እንደ ሀገር ኢትዮጵያ እንደ ቤተክርስቲያንም የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ነች። ቢያንስ በቅዳሴ ላይ ሰባኪ ያልቆመባቸው፣ ወንጌል ያልተሰማባቸው፣ ሃይማኖት አበው የማይነበብባቸው ገዳማትና አብያተክርስቲያናት የሉም። ስለዚህ ስብከት መንዘፍዘፍና ዓላማ የሌለው ጩኸት አይደለም። በእርጋታ፣ በማስተዋል፣ በጥንቃቄ የሚፈጸም በብዙ ዓይነት መንገድ የሚከናወን፤ ያልነበሩትን የምናመጣበት የነበሩትን የምናጸናበት አገልግሎት መሆኑን ሁሉም ይረዳ።
በዲ/ን እሸቱ
ሚያዝያ 26፣2003ዓ.ም
ሰው ማነው? ብሎ ለጠየቀ “ሰው ንግግሩን ይመስላል” እንዳትለኝ ንግግሩ እምነቱን የሚያመለክት ዕውቀት አይሆነውምና ነው፡፡ ለሰው ባሕርያዊ ተፈጥሮና ዕውቀት ምስክሩ ውስጣዊ የአዕምሮ አቋምና የሕሊና ሕግ ነው ብለንም አንደመድምም፡፡ ሰው እንዲያውቅ የተመደበለት የሕግ ተፈጥሮ ዕውቀት መጀመሪያ ክፍል መልካምን ማወቅ፡፡ ሁለተኛ ክፋትን ንቆ መልካምን ገንዘብ ማድረግ፡፡ ሦስተኛ መልካምን በግብር መግለጽ ናቸው፡፡ የቤተ ክርስቱያን ሊቃውንት ይሁዳን ሲገልጹ “በአፍ አምኖ በልቡ የካደ” ይሉታል፡፡ ባህላችን “አፈ ቅቤ፤ ሆደ ጩቤ” እንዲል፡፡
የክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር መሠረት ያለ ትምህረት በተፈጥሮ የሚሰጥ ሲሆን ይህም ሕገ ልቦና፤ ሕገ ህሊና፤ ሕገ ተፈጥሮ ወይንም ሕገ ጠብዓያዊ በመባል ይታወቃል፡፡ ሕገ ኦሪትና ሕገ ወንጌል፤ ሕገ ሕሊናን ይተረጉማሉ፡፡ ለአብነት ብንጠቅስ አዳምና ሔዋን ቅዱስ ዳዊትና ይሁዳን፤ ከመጸጸት ክፉዎችን ከማዘን የምታደርሳቸው የሕሊና ኮሽታ ነች፡፡ በኑሮ ሂደት ሀዘን፣ ጸጸት ርትዕ በምናደርግበት ጊዜ ልዩ መንፈሳዊ ጥበብ አልያም ዕውቀት በመታደል ሳይሆን ሰው በመሆናችን በሕሊና ውስጥ የተቀረጸ በህሊና ሚዛን የሚሰጥ ፍርድ በመኖሩ ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ሕገ ሕሊና በጽሑፍ ከተሰጡን ሕግጋት /ሕገ ኦሪት፣ ሕገ ወንጌል፣ ማሕበራዊ ሕግ/ በላይ ሰማያዊና ምስጢርን ለመጠበቅ ሲያገለግል እናገኘዋለን፡፡ የቤተ ክርስቲያን የሀገር የግል ምስጢር ይጠበቅ ዘንድ መንፈሳዊ ሕግና ማህበረሰባዊ ሕግ ይደነግጋል፡፡ የአምላክ እናት ድንግል ማርያም ያለ ምድራዊ ሕግ አስገዳጅነት በሕገ ልቦና ዳኝነት ለሰማያዊ ምስጢር የታመነች ነበረች “እናቱ ማርያም በልቧ ትጠብቀው ነበር” እንዲል፡፡ /ሉቃ.2÷19/፡፡
“ሰው ራሱ መጽሐፍ ነው” የሚለው የአነጋገር ስልት የሚያስተላልፈው ሰው ይነበባል፤ ይጠናል፤ ይተነተናል ይጸድቃል፤ ይሻራል ለማለት ነው፡፡ እነዚህን ተግባራት ለሌሎችም ሆነ ለራሳችን ለድርጊታችን ብያኔ ፍርድ ለመስጠት ረቂቅ የሕሊና ልጓም እንደ መሠረት ሆኖ ያገለግላል፡፡ ሰው በውስጡ የሚያረጋግጣት እውነት በክበበ አዕምሮ በሚጨበጥ ሕገ ባሕርይ ከመገለፅ እምቢ አትልም፡፡ እግዚአብሔርን ደስ ለማሰኘት እምነት በቅድሚያ እንዲገኝ ግድ ቢሆንም በተግባር ወይንም በድርጊት ካልተዋሃደ ክርስቲያናዊ ሕይወታችን ፍሬ ቢስ፤ ረብ የሌለው ከንቱ ድካም ይሆናል፡፡ ለመሆኑ እምነታችን ከድርጊታችን ለምን ተዛነፈ? በጽናት የምናምነውን እምነት አጥቦ የመውሰድ ብቃት ያለው ሃይል ይኖር ይሆን? በዕለት ተዕለት ማኅበራዊ መስተጋብር የምንወስናቸው መጠነ ሰፊ ጥቃቅን ውሳኔዎች ውህደ ሃይማኖት ምግባር የታሹ ወይስ የስሜት ውጤቶች ናቸው? እርግጥ ነው ስሜት አልባ ሰብአዊ ፍጡር ሊሆን አይችልም፡፡ ነገር ግን ነፍስን ደስ የሚያሰኝ ሰማያዊ እውነት ከስሜት በላይ ነው፡፡ በገሃዱ ዓለም በብዙዎቻችን ሕይወት የሚታየው ውሳኔዎቻችን በድካም ባካበትነው ዕውቀት፤ መንፈሳዊ አስተምህሮ፤ ዓለማዊ ጥበብ፤ የቅዱሳን ሕይወት ሳይሆን ለስሜት ያጋደለ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ለሁለት ጌታ መገዛት አይቻልም የሚለውን ኃይለ ቃል ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የተማረው ይሁዳ ለ30 ብር ሸጦታል ለምን ትለኝ እንደሆን ሰው ክፉን ነገር እስኪሰራ ሰው ልበ ሙሉ ይሆናልና ነው፡፡ ሁለተኛው የህሊና ዓይን ከነፍስ ባይለይም በኃጢአት ምክንያት ይጨልማል ይደክማልና ነው፡፡ በአጭር አገላለጽ ድርጊታችንን የሚቆጣጠረው በዕለቱ ስሜታችንን ያቀጣጠለው ኃይል እንጂ በጥረት ያካበትነው ትምህርት ወይም ዕውቀት ሆኖ አይታይም፡፡ ሰው ሆይ ለምን ይሆን…
የጥናትና ምርምር ማዕከሉ ዳይሬክተር ዲ/ን መንግስቱ ጎበዜ እንደገለጹት ዓመታዊ ዓውደ ጥናቱ “ጥናትና ምርምር ለቤተ ክርስቲያን አስተዳደር መጠናከር” በሚል መሪ ቃል ይከናወናል።
የዓውደ ጥናቱ ዋና ዓላማም መሠረታዊ ችግሮችን በመለየትና የመፍትሔ አቅጣጫዎችን በመጠቆም የቤተ ክርስቲያንን አስተዳደር ለማጠናከር ይረዳ ዘንድ ነው ብለዋል።
በሁለቱም ቀናት አምስት ጥናቶች የሚቀርብ ሲሆን፥ የመንፈሳዊ ፍርድ ቤት አስፈላጊነት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ የሰው ኃይልና የገንዘብ አስተዳደር ሥርዐት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ የውጭ ሀገር ሰዎች ተደራሽነት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ ነገረ ማርያም በድርሳነ ጽዮን፣ እንዲሁም ይምርሃነ ክርስቶስ ዘመን ተሻጋሪው ሥልጣኔ የሚሉት ርዕሶች ተመርጠው እንደቀረቡ ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።
ጥናቶቹ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በሚያስተምሩ ምሁራንና ሌሎች ተመራማሪዎች የተዘጋጁ ሲሆን የውይይት መሪዎችም ከጉዳዩ ጋር ዝምድና ያላቸው ታዋቂ ምሁራን መሆናቸው ተገልጿል። በዓውደ ጥናቱ ላይ መሳተፍ ለሚፈልጉ ሁሉ እንዲገኙ ዳይሬክተሩ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።
በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት በብሉያትና በሐዲሳቱም የምትነሣው ሣራ አበ ብዙኃን ሥርወ ሃይማኖት የምንለው የአብርሃም ሚስት ነች፡፡ እግዚአብሔር ለአብርሃም የብዙዎች አባት እንዲሆን ቃል ኪዳን ሳይገባለት በፊት፣ በመካንነት ታዝን፣ ተስፋም አጥታ ትተክዝ በነበረችበት ጊዜ ሦራ ትባል ነበር፡፡
ሦራ ሙቀት ልምላሜ ከተለያት በኋላ ልጅ እንደምትወልድ ከአብርሃም በኩል እግዚአብሔር ቃል ኪዳን ከገባላት፣ ተስፋም ከተሰጣት በኋላ ሣራ ተብላለች፡፡ እግዚአብሔርም ስለእርሷ ለአብርሃም «የሚስትህን የሦራን ስም ሦራ ብለህ አትጥራ፤ ስምዋ ሣራ ይሆናል እንጂ፤ እባርካታለሁ፤ ደግሞም ከእርሷ ልጅ እሰጥሃለሁ፤ እባርካትማለሁ፤ የአሕዛብ እናት ትሆናለች፤ የአሕዛብ ነገሥታት ከእርሷ ይወጣሉ» በማለት ተናገረው /ዘፍ. 17፥15/፡፡
ሣራ ሦራ ተብላ ትጠራ በነበረበት፣ ያለተስፋ በኖረችበት የቀደመው ዘመኗ ለአብርሃም ልጅ አልወለደችለትም ነበር፡፡ ሦራ ዘር ማጣት ታላቅ ሐዘን በሆነበት በዚያ ዘመን፣ መካንነት ያስንቅ በነበረበት በዚያን ጊዜ አብራም ከሌላ ይወልድ ዘንድ አዘነችለት፡፡ አብራም አጋር ወደ ተባለችው ግብጻዊት ባሪያዋ ይደርስ ዘንድ «እነሆ እንዳልወልድ እግዚአብሔር ዘጋኝ ምናልባት ከእርሷ በልጅ እታነጽ እንደ ሆነ ወደ እርሷ ግባ» አለችው፡፡ /ዘፍ.16፥2/ በትሑቷ ሦራ ምክር አጋር ከአብርሃም በፀነሰችበት ወራት ሦራን አሳዘነቻት፤ አጋርም ተመካች፤ እመቤት የነበረችውን ሦራ ስለመካንነቷ በዓይኗ አቃለለቻት፡፡ ይህ ለሦራ በእግዚአብሔር እና በባሏ በአብራም ፊት ያዘነችበት ሰቆቃዋ ነው፡፡ ሦራም ከሐዘኗ ጽናት የተነሣ አብራምን እንዲህ አለችው «መገፋቴ በአንተ ላይ ይሁን እኔ ባሪያዬን በብብትህ ሰጠሁህ፤ እንዳረገዘችም ባየች ጊዜ እኔን በዓይኗ አቃለለችኝ፤ እግዚአብሔር በእኔና በአንተ መካከል ይፍረድ» አለችው፡፡ በአብራም ፍርድም ሦራ ባሪያዋን አጋርን በመቅጣቷ አጋር ኮበለለች፡፡
እንግዲህ ከላይ አስቀድመን የጠቀስነው ለአብርሃም የተገባው ቃል ኪዳን የተሰጠው ሦራና አብራም በዚህ ሐዘን ውስጥ በነበሩበት ጊዜ ነው፡፡ ያዘነችው ሦራ ከቃል ኪዳኑ በኋላ የብዙኃን እናት ልትሆን ሣራ ተብላ እርሱም የብዙዎች አባት ሊሆን አብርሃም ተብሎ የተስፋው ቃል ተነገረው «በእውነት ሚስትህ ሣራ ወንድ ልጅን ትወልድልሃለች ስሙንም ይስሐቅ ብለህ ትጠራዋለህ ከእርሱ በኋላ ለዘሩ የዘላለም ቃልኪዳን እንዲሆን ቃል ኪዳኔን ከእርሱ ጋር አቆማለሁ» /ዘፍ.17፥19/፡፡
እግዚአብሔር ለአብርሃም ሣራ እንደምትወልድ የነገርውን የተስፋ ቃል በቤቱ በእንግድነት ተገኝቶ አጸና፡፡ «የዛሬ ዓመት እንደ ዛሬው ጊዜ ወደ አንተ በእውነት እመለሳለሁ ሚስትህ ሣራም ልጅን ታገኛለች፡፡»/ዘፍ.18፥10/ አለው፡፡ ሁል ጊዜም ቃሉ የሚታመን እግዚአብሔር ይመስገንና እንደተባለው ሆነ «እግዚአብሔርም እንደተናገረው ሣራን አሰበ እግዚአብሔርም እንደተናገረው ለሣራ አደረገላት ሣራም ፀነሰች እግዚአብሔርም በተናገረው ወራት ለአብርሃም በእርጅናው ወንድ ልጅን ወለደችለት አብርሃም ሣራ የወለደችለትን የልጁን ስም ይስሐቅ ብሎ ጠራው» /ዘፍ.21፥1/ «ሣራም እግዚአብሔር ሳቅ /ደስታ አድርጎልኛል ይህንንም የሚሰማ ሁሉ በእኔ ምክንያት ይስቃል አለች ደግሞም ሣራ ልጆችን እንድታጠባ ለአብርሃም ማን በነገረው በእርጅናው ልጅን ወልጄለታለሁና /ዘፍ. 21፥7/፡፡
እንግዲህ መካኒቱ ሣራ ሙቀት ልምላሜ ከተለያት በኋላ በጨዋነት ወልዳ ለአብርሃም ለዘላለም የገባው ቃል ኪዳን የሚፈጸምበትን ዘር ይስሐቅን አሳድጋለች፡፡ በቃል ኪዳን፣ በተስፋ የተወለደው ይስሐቅ ታላቅ ነውና «የዚህች ባሪያ /የአጋር/ ልጅ ከልጄ ከይስሐቅ ጋር አይወርስም» አለች፡፡ እግዚአብሔርም ቃሏን ተቀብሎ ለአብርሃም «ሣራም የምትነግርህን ቃል ሁሉ ስማ በይስሐቅ ዘር ይጠራልሃልና…» አለው /ዘፍ.21፥1-12/፡፡
እንዲህ በእግዚአብሔር የተስፋ ቃል የከበረችው ሣራ በብሉያት ብቻ ሳይሆን በሐዲሳትም ለተለያዩ ጉዳዮች እንደ አርአያና ምሳሌ ስትጠቀስ እናነባለን፡፡ ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ ሚስቶችን ሲመክር በመልካም ትሑት ሰብእናዋ አርአያ የምትሆን አድርጎ የጠቀሳት ሣራን ነው «ጠጉርን በመሸረብ፣ ወርቅን በማንጠልጠል፣ ወይም ልብስን በመጎናጸፍ በውጪ በሆነ ሽልማት» ሳይሆን «በእግዚአብሔር ፊት ዋጋው እጅግ የከበረ የዋህና ዝግተኛ መንፈስ ያለውን የማይጠፋውን ልብስ» ተጎናጽፋ ውስጧን ያስጌጠች ብፅዕት ሚስት መሆኗን መስክሯል፡፡ «ሣራ ለአብርሃም ጌታዬ ብላ እየጠራችው ታዘዘችለት፤ እናንተም ከሚያስደነግጥ ነገር አንዳች እንኳ ሳትፈሩ መልካም ብታደርጉ ልጆችዋ ናችሁ፡፡» /1ጴጥ. 3፥3-6/ ብሏል፡፡
ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ የክርስቶስ የማዳኑ የምስራች ከታወጀላቸው በኋላ ሕገ ኦሪትን ካልጠበቅን አንድንም የሚሉ ቢጽሐሳውያንን ቃል ሰምተው ያመኑ የገላትያን ሰዎች በገሰጸበት መልእክቱ ሣራን የሕገ ወንጌል ምሳሌ አድርጎ አቅርቧታል፡፡ በአንጻሩ ባሪያዋን አጋርን የሕገ ኦሪት ምሳሌ አድርጎ አቅርቧል /ገላ.4፥21/፡፡
የሣራን ሕይወት በዚህ ጽሑፍ ያነሣንበትንም መሠረታዊ ምክንያትም ይህንን የቅዱስ ጳውሎስን ምሳሌያዊ መልእክት ተንተርሰው ያለአገባቡ እየጠቀሱ የቤተ ክርስቲያናን ልጆች ምእመናንን ግራ ስለሚያጋቡ የተሐድሶ መናፍቃንና ተሐድሶአዊ ትምህርት ስለሚያስተምሩ ሰዎች ሐሳብ ለማንሣት ነው፡፡ በቅድሚያ የቅዱስ ጳውሎስ የመልእክቱን ሐሳብ በአጭሩ እናብራራና፤ ተሐድሶ የዘመቻ ማወራረጃ አድርጎ ስለሚጠቀምበት ጥራዝ ነጠቅ ቃልና አስተሳሰብ ደግሞ ቀጥሎ እናመጣለን፡፡ ሐዋርያው ስለዚህ ነገር ሲናገር የሚከተለውን ብሏል፡፡
«እናንተ ከሕግ በታች ልትኖሩ የምትወዱ ሕጉን አትሰሙምን ? እስኪ ንገሩኝ፤ አንዱ ከባሪያዪቱ አንዱ ከጨዋዪቱ የሆኑ ሁለት ልጆች ለአብርሃም እንደነበሩት ተጽፏልና፤ ነገር ግን የባሪያዪቱ ልጅ እንደ ሥጋ ተወልዷል፤ የጨዋዪቱ ግን በተስፋው ቃል ተወልዷል፤ ይህም ነገር ምሳሌ ነው እነዚህ ሴቶች እንደ ሁለቱ ኪዳናት ናቸውና፤ ከደብረ ሲና የሆነችው አንዲቱ ለባርነት ልጆችን ትወልዳለች፤ እርሷም አጋር ናት፤ ይህቺም አጋር በዓረብ ምድር ያለችው ደብረ ሲና ናት፤ አሁንም ያለችውን ኢየሩሳሌምን ትመስላለች፤ ከልጆቿ ጋር በባርነት ናትና፤ ላይኛዪቱ ኢየሩሳሌም ግን በነጻነት የምትኖር ናት፤ እርሷም እናታችን ናት… ስለዚህ ወንድሞች ሆይ የጨዋዪቱ ልጆች ነን እንጂ የባሪያዪቱ አይደለንም» /ገላ.4፥21-31/፡፡
በገላትያ መልእክቱ ቅዱስ ጳውሎስ ትኩረት የሰጠው ጉዳይ «የክርስቶስን ሐዋርያት እንዲመስሉ ራሳቸውን እየለወጡ ውሸተኞች ሐዋርያትና ተንኮለኞች ሠራተኞች» ስለነበሩት ከአይሁድ ወገን የሆኑ ካልተገረዛችሁ፣ ሕገ ኦሪትንም ካልፈጸማችሁ አትድኑም እያሉ የሚያስተምሩ ሰዎች ጉዳይ ነው፡፡ እነዚህ ኦሪታዊ ሁኑ የሚሉ ሰዎችን ትምህርት እየሰሙ የወንጌልን ቃል ቸል ያሉት የገላትያን ሰዎች በግልጽ «እግዚአብሔርን ስታውቁ፣ ይልቅስ በእግዚአብሔር ስትታወቁ እንደገና ወደ ደካማ ወደሚናቅም ወደ መጀመሪያ ትምህርት እንዴት ትመለሳላችሁ? እንደገና ባሪያዎች ሆናችሁ ዳግመኛ ለዚያ ልትገዙ ትወዳላችሁን ? ቀንና ወርን ዘመንንም ዓመትንም በጥንቃቄ ትጠብቃላችሁ…» ይላቸዋል፡፡ /ገላ.4፥9-11/
የሐዋርያው ዋነኛ ጉዳይ ሕገ ኦሪት ይጠበቅ አይጠበቅ በመሆኑም ነው «እናንተ ከሕግ በታች ልትኖሩ የምትወዱ ሕጉን አትሰሙምን ?» ያላቸው /ገላ. 1፥21/፡፡ ምክንያቱም ያመኑትን ሁሉ በደሙ የዋጀ የኢየሱስ ክርስቶስ የምስራች ወንጌል ከተነገረች በኋላ ዳግመኛ ወደ ኋላ ተመልሶ ቀንና ወርን ዘመንንም እየቆጠሩ መሥዋዕተ ኦሪትን ለማቅረብ፣ ግዝረትን አበክሮ ለመጠበቅ፣ ያንንም ካልፈጸማችሁ አትድኑም ወደሚል ትምህርት መመለስ ያሳፍራልና፡፡
ስለዚህ እናንተ በኦሪት እንኑር የምትሉ ሆይ! በኦሪት የተነገረውን ምሳሌ አንብቡ ብሎ የሣራን እና የአጋርን ምሳሌነት ያነሣል፡፡ በኦሪት አብርሃም አስቀድመን እንዳየነው ጨዋይቱ ከተባለችው ከእመቤቲቱ ሣራ ይስሐቅን፣ ከባሪያይቱ ከአጋር ደግሞ እስማኤልን ወልዷል፡፡ የሁለቱ ልደት ግን ለየቅል መሆኑን ይነግራቸዋል፡፡ ከባሪያዪቱ የተወለደው አጋር ሙቀት ልምላሜ እያላት ተወልዷልና፤ ከእመቤቲቱ የተወለደው ግን ሙቀት ልምላሜ ከተለያት በዘጠና ዓመቷ/ ከእግዚአብሔር ብቻ በተሰጠው ተስፋ ተአምራትም ተወልዷልና፡፡ እነዚህ ሁለቱ ሴቶች የሕገ ኦሪትና የሕገ ወንጌል ምሳሌ ናቸው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም በቃሉ «ይህም ነገር ምሳሌ ነው» እንዳለ /ገላ. 4፥24/፡፡ አጋር ኦሪትን ደብረ ሲናን አንድ ወገን ያደርጋል፤ ሣራን፣ ወንጌልን ሰማያዊቱ ኢየሩሳሌምን ደግሞ አንድ ወገን እያደረገ እያነጻጸረ ተናግሯል፡፡
አንዲቱ /ኦሪት/ አምሳል መርገፍ ሆና በደብረ ሲና ተሠርታለችና፤ ደብረ ሲናም ከኢየሩሳሌም ስትነጻጸር በምዕራብ ያለች ተራራ ናትና፤ ስለዚህ ይህች ምድራዊት የምትሆን አምሳል መርገፍ አማናዊት ከምትሆን ሰማያዊት ኢየሩሳሌም ጋር ስትነጻጸር ዝቅ ያለች ናትና «ወትትቀነይ ምስለ ደቂቃ» አምሳል መርገፍ በመሆን ከልጆቿ ጋር ትገዛለች፡፡ ላዕላዊት የምትሆን ኢየሩሳሌም ግን ከመገዛት ነጻ ናት ብሎ «ወይእቲ እምነ፤ እርስዋም እናታችን ናት» ይላል፡፡ ይቺም እናታችን ሣራ ምሳሌዋ የምትሆን ወንጌል ናት፡፡
ስለዚህ ከሣራ የተወለደው ተስፋውን ወራሽ እንደሆነ ሁሉ እኛም ከወንጌል የተወለድን ክርስቶሳውያን በይስሐቅ አምሳል እንደይስሐቅ ተስፋውን መውረስ የሚገባን የነጻነት ልጆች ነን ማለቱ እንደሆነ ሊቃውንቱ ያስተምራሉ፡፡ የባሪያዪቱ ልጅ ከእመቤት ልጅ ጋር ተካክሎ ርስት አይወርስምና በበግና በፍየሎች ደም ምሳሌያዊ ወይም ጥላ አገልግሎት በምትሰጥ ገረድ /ሞግዚት/ የተባለች የኦሪት ልጆች አይደለንም፡፡ ክርስቲያኖች በእግዚአብሔር ልጅ ሥጋና ደም ነጻ በምታወጣ አዲስ ኪዳን የወንጌል ልጆች ነንና፡፡
ሐዋርያው ይህንን ሁሉ ያለው ካልተገረዛችሁ አትድኑም የሚለውን የቢጽ ሐሳውያንን ትምህርት በመኮነን ሲሆን ይህንንም በግልጽ «በክርስቶስ ኢየሱስ ሆኖ በፍቅር የሚሠራ እምነት እንጂ መገረዝ ቢሆን ወይም አለመገረዝ አይጠቅምምና /ገላ. 5፥6/ ይላል፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ ሆኖ በፍቅር የሚሠራ ያለው ሕይወትም ፍትወተ ሥጋን አሸንፎ በመንፈሳዊ ተጋድሎ የበቁ ሆኖ በመንፈስ መራመድን ነው፡፡ ይህ ሣራ በተመሰለችባት ሕገ ወንገል ውስጥ የተጠራንበት የመታዘዝ ሕይወት ነው፡፡ ሐዋርያውም ለገላትያ ሰዎች ይህንኑ ተርጉሞ ሲናገር «የክርስቶስ ኢየሱስም የሆኑት ሥጋን ከክፉ መሻቱና ከምኞቱ ጋር ሰቀሉ» /ገላ. 5፥24/ አለን፡፡ ስለዚህ የቤተክርስቲያን ወገኖች ሁሉ ሥጋን ከክፉ መሻቱና ከምኞት ጋር የሰቀሉ መንፈሳውያን፣ በፍቅር የእግዚብሔርን ትዕዛዝ የሚፈጽመው የጨዋይቱ /የእመቤቲቱ/ የሣራ ልጆች ናቸው፤ እንጂ ሥጋዊ ሥርዓት፣ መርገፍ፣ ጥላ በሆነው ብሉይ ኪዳን ውስጥ የመገረዝ አለመገረዝ ጣጣን የሚሰብኩ፣ የሚሰበኩ በሥጋ ልማድ የወለደችው የባሪያዪቱ የአጋር ልጆች አይደሉም፡፡
እንግዲህ በነጻነት የምትመራውን ላይኛይቱን ኢየሩሳሌምን የመረጡ ክርስቶሳውያን ለ2ሺሕ ዘመናት ያህል ክርስቶስን በመስበክ በስሙም ክርስቲያን ተብለን ስንጠራ ኖረናል፡፡ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች ገና አስቀድሞ በ34 ዓ.ም «ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ አምናለሁ፡፡ ካለው ጃንደረባው ጀምረው ሠልጥና ከነበረችው ባሪያይቱ አጋር ይልቅ በተስፋው ሥርዓት የወለደችውን እመቤቲቱን ሣራ መርጠው እስከዚህ ዘመን ድረስ ኖረዋል፡፡
ከየካቲት ወር 1990 ዓ.ም ጀምሮ ግን «ተሐድሶ» በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ላይ በይፋ በጀመረው ዘመቻ ውስጥ የዘመቻው አዋጅ ማጠንጠኛ «አሮጊቷ ሣራ እኔ /እኛን/ ወለደች» የሚለው ቃል ነው፡፡ «የተሐድሶ መነኮሳት ኅብረት» የተባለው ቡድን በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ሆኖ ከቤተ ክርስቲያን ማዕድ እየተቋደሰ ነገር ግን በመሠሪነት ለመናፍቃን ተላላኪ ሆኖ የቆየ ሲሆን በየካቲት ወር 1990 ግን በአዲስ አበባ ከተማ በኢግዚብሽን ማዕከል በፕሮቴስታንቶች ተደራጅቶ በተዘጋጀው «ጉባኤ» በይፋ ራሱን ለይቶ የ«ተሐድሶ» ጥሪ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ላይ እንዲደረግ ሲያውጅ ተገኝቷል፡፡ /ይህንን ለማጋለጥ የወጣወን ቪዲዮ ፊልም ወይም ቪሲዲ ይመልከቱ/ በዚህ አዋጅ በጉልህ የሚስማው ድምፅ ከላይ የተጠቀሰው «አሮጊቷ ሣራ እኔን ወለደች» የሚለው ንግግር ነበር፡፡ ይህንን ቃል ደጋግሞ ሲያስተጋባ የነበረው አባ ዮናስ /በለጠ/ የተባለው «መነኩሴ» «ወንጌልን ለመስበክ ተሾምኩ፤… አሮጊቷ ሣራ ወለደች፤ አሮጊቷ ሣራ እኔን ወለደች፣ ዘውዱን ወለደች፣ ፍስሐን ወለደች፣ ገብረ ክርስቶስን ወለደች… ይህ ትውልድ የኢያሪኮን ግንብ ያፈርሳል…» ወዘተ እያለ አብረውት ለጥፋት የተሰለፉ ከሃዲ መነኮሳትን እየጠቀሰ ፎክሯል፡፡
በእነ አባ ዮናስ አዋጅ ውስጥ ያለው ግልጽ መልእክት ግን በሁለት መልኩ የሚታይ ወይም ሊተረጎም የሚችል ነው፡፡
1. ቤተክርስቲያንን በእርጅና ዘመኗ ከወለደችው ከቅድስት ሣራ ጋር በማነጻጸር ራሳቸውን የዚህችው ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን አድርገው በማቅረብ ከዚህች ቤተክርስቲያንም አካል የተገኙ መሆናቸውን በመግለጥ የቤተክርስቲያን አስተምህሮ እነርሱ የሚሉት እንደሆነ አድርገው ለማደናበር ነው፡፡
2. ሌላው የድፍረት መልእክት ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን በባሪያይቱ በአጋር ምሳሌ ልትጠቀስ የምትችል ኦሪታዊት፤ የጨዋይቱ የተባለች የሣራ የተስፋው ዘር ቅሪት የሌለባት፣ የወንጌል ብርሃን ያልበራባት፤ ክርስቶስን የማታውቅ፣ ጌትነቱንም የማታምን አድርገው አቅርበዋታል፡፡ ራሳቸውንም ለኢትዮጵያ ሕዝብ ወንጌልን ለማድረስ የተሾሙ በኩራት አድርገው አቅርበዋል፡፡
የመጀመሪያውን ትርጉም ወይም መልእክት በማጉላትም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስም የዚህን የ«ተሐድሶ» መሠሪ አካሔድ በውል በመረዳት አውግዞ በመለየትና ውግዘት በማስተላለፍ ለ2ሺሕ ዘመናት ወንጌልን ስትሰብክ የነበረች ቤተ ክርስቲያንን ልዕልናና ክብር አጉድፎ በወንጌል ሰባኪነት ስም በማጭበርበር ፕሮቴስታንታዊ ኑፋቄ ለመዝራት ተሐድሶ እያደባ መሆኑን አጋልጧል፡፡ ጠቅላይ ቤተክህነት ከሰጠው ሰፊ መግለጫ ውስጥ ይህን የተመለከተውን በአጭሩ እንደሚከተለው እናስታውስ፡፡
«አሮጊቷ ሣራ ወለደች» የሚል ኃይለ ቃል መናገራቸው ተዘግቧል፤ መናፍቃኑ ይህን የተናገሩት የእነሱን ከጥንታዊቷ ቤተ ክርስቲያናችን አፈንግጦ መውጣት የዘጠና ዓመት እድሜ ከነበራት እና ከቅድስት ሣራ ከተወለደው ከይስሐቅ ልደት ጋር ለማነጻጸር በመፈለግ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡
የይስሐቅ እናት ቅድስት ሣራ በመሠረቱ እናትና አባቱን የሚያከብርና የሚያስከብር እንጂ የሚያዋርድ፣ እናትና አባቱን የሚያስመሰግን እንጂ ሰድቦ የሚያሰድብ፣ በእናትና አባቱ እግር የሚተካ እንጂ እናትና አባቱን የሚክድ፣ በወላጆቹ የተመረቀ እንጂ የተረገመ ልጅ እናት አይደለችም፡፡
በቅድስት ሣራ አምሳል የተጠቀሰችው ጥንታዊቷ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም እንዲሁ እናቱን ለመሸጥና ለመለወጥ የሚያስማማ፣ እናቱን ሲሰድብና ሲነቅፍ ሐፍረት የማይሰማው ርጉም ልጅ እናት አይደለችም፤ ቤተ ክርስቲያናችን እንዲህ ያለ ልጅ አልወለደችም፣ አትወልድምም፡፡
ጠላትና አረም ሳይዘሩት ይበቅላል እንደሚባለው፣ በአንድ የስንዴ ማሳ ላይ የበቀለ አረም ቢኖር ያ አረም ሳይዘራ የበቀለ መሆኑን ማረጋገጥ አስቸጋሪ እንደማይሆን ሁሉ እነዚህ መናፍቃንም በቤተ ክርስቲያናችን የስንዴ ማሳ ላይ ሳይዘሩ የበቀሉ ጠላቶች እንደሆኑ መገንዘብ አስቸጋሪ አይሆንም፡፡ በምሳሌ ዘር እንደተጠቀሰው /ማቴ.13፥24-30/ በንጹሕ ስንዴ ማሳ ላይ ጠላት የዘራው ክርዳድ ሊበቅል እንደሚችልም ታውቋል፡፡ እነዚህ መናፍቃንም የጠላት እንጂ የቤተ ክርስቲያናችን አበው ተክል ባለመሆናቸው ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እንደ ተወለዱ አድርገው ራሳቸውን ከማስተዋወቅ ይልቅ የማን ልጆች እንደሆኑ ቢጠይቁ ዕውነቱን ለማወቅ በቻሉ ነበር፡፡
አሁንም ቢሆን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ በጻፈው ሁለተኛ መልእክቱ «በኋላ ዘመን አንዳንድ ሰዎች ገንዘብን የሚወድዱ፣ ራሳቸውን የማይገዙ፣ ሐሜተኞች፣ መልካም የሆነውን ነገር ሁሉ የማይወዱ ከዳተኞች ይሆናሉ፤ የአምልኮት መልክ አላቸው፤ ኃይሉን ግን ይክዱታል፤ ከእነዚህ ደግሞ ራቅ ወደ ቤቶች ሾልከው እየገቡ ኃጢአታቸው የተከመረባቸውን በልዩ ልዩ ምኞትም የሚወሰዱትን፣ ሁልጊዜም እየተማሩ እውነትን ወደ ማወቅ ከቶ ሊደርሱ የማይችሉትን… የሚማርኩ ከእነዚህ ዘንድ ናቸውና» /1ጢሞ. 3.1-7/ ሲል እንደተናገረው እነዚህ መናፍቃን ከዚህ የትንቢት ዘመን የተወለዱ እንጂ የቤተ ክርስቲያናችን ልጆች አለመሆናቸውን በግልጽ መንገር ግዴታ ይሆናል፡፡ /መጋቢት 26 ቀን 1990 ዓ.ም/
ጠቅላይ ቤተክህነት የተነተነበት መንገድ እንዳለ ሆኖ የ«ተሐድሶ» ቡድን «አሮጊቷ» የሚለውን ቃል የመረጠበትን መሠረታዊ ምክንያት በውል ማጤን ይገባል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ወንጌልን የምትሰብክን ቤተ ክርስቲያን ከቅድስት ሣራ ጋር አነጻጽሮ ባቀረበበት መንገድ አስበው ተናግረውት ቢሆንማ ከኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን አፈንግጠው የፕሮቴስታንት ፓስተሮች ባዘጋጁት በዚያ የስድብ ጉባኤ ላይ የቤተ ክርስቲያኒቱን የሃይማኖት ትምህርትና ሥርዓት የምእመ ናንን ሕይወት ባላዋረዱ ባላናናቁ ነበር፡፡ ነገር ግን «አሮጊት /አሮጌ» የሚለውን ቃል የመረጡት ቤተ ክርስቲያን አርጅታለችና ማደስ አለብን ለሚለው አስተሳሰብ መንደርደሪያ ነው፡፡ እነዚህ የተሐድሶ መናፍቃን ተወግዘው ቢለዩም በውጪም በውስጥም ሆነው ቤተ ክርስቲያንን ለመገዝገዝና አስተምህሮአቸውን አንዳንድ የቤተ ክርስቲያኒቱ «መምህራን» አውቀውም ሳያውቁም በየዓውደ ምህረቱ እንዲያስተጋቡ ተፅዕኖ መፍጠራቸውን ቀጥለዋል፡፡
እነ አባ ዮናስ የ«አሮጊቷ ሣራ ወለደች» ቃላቸውን ከአዋጁ ከ12 ዓመታት በኋላ አሁን በይፋ ደግሞ «ቤተ ክርስቲያንን አሪታዊት፣ ጨለማ ውስጥ ናት ሲሉ አሮጊቷ ሣራ ዛሬ እኔን ወለደች፣ እገሌን ወለደች፣ እገሌን ወለደች…» የሚል ከእነ አባ ዮናስ ጋር የቃልና የስሜት ዝምድና ያለው የአዋጅ ቃል በአንዳንድ ሰባኪያን ነን ባዮች ተሰምቷል፡፡ በአባ ዮናስና በእነዚህ ሰባኪያን መካከል ያለው የአቀራረብ ልዩነት የአባ ዮናስ በኤግዚቢሽን ማዕከል፣ እነዚህ ደግሞ በራሷ በቤተ ክርስቲያኒቱ ዓውደ ምህረት ላይ ማወጃቸው ነው፡፡
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ያስተማረው ትምህርት ቃሉም ትርጓሜውም የታወቀ ሆኖ ሳለ ቤተ ክርስቲያናችንም ከጨዋይቱ የተወለድን ክርስቲያኖች አንድነት መሆኗ ለ2ሺሕ ዘመን የተመሰከረ ሆኖ ሳለ የአሁኖቹ «ሰባክያን» ራሳቸውንና ጓደኞቻቸውን ነጥለው «የተስፋው ወራሾች የአሮጊቷ የሣራ ልጆች» እያሉ የሚያቀርቡበት ገለጻ ትርጓሜ ይፋ መሆን አለበት፡፡
በመሠረቱ በሐዋርያው በቅዱስ ጳውሎስ የተሰበከውን ምሳሌያዊ ትምህርት ይዞ ተንትኖ ማስተማር ተገቢ ነው፡፡ ነገር ግን ከአርባ ሚሊዮን በላይ ምእመናን ባሉበት ጥንታዊት እና ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ራሳቸውንና እነርሱ የመረጧቸውን የቡድን አባላት አባ ዮናስ ባቀረቡበት መንገድ «የአሮጊቷ ሣራ» ብሎ የጠሩበት ቤተ ክርስቲያን እነርሱን ከመውለዷ በፊት ምን ጎድሎባት፣ ምንስ አጥታ ነበር ? ቅዱስ ጳውሎስ መካኒቱ፣ ጨዋይቱ፣ እመቤቲቱ እያለ የጠራበት ቅጽል እያለ «አሮጊቷ» የሚለውን በማስጮኽ ማቅረብስ ለምን ተፈለገ ? ቀጥተኛ ምንጩስ ማነው ? ምንድነው ? እነዚህ ሁሉ ጥያቄዎች መመለስ ያለባቸው ናቸው፡፡ እነ አባ ዮናስ «አሮጊቷ ሣራ» ያሏትን ቤተ ክርስቲያንን ድንግል ማርያምን፣ ተክለሃይማኖትን፣ ጊዮርጊስን በልብሽ አኑረሻልና አውጪ እያሉ በአደባባይ ድፍረት ተናግረዋል፡፡ በእነዚህ «ሰባክያን» የ«አሮጊቱ ሣራ» አስተምህሮ ውስጥ ያለው አንድምታስ ምንድነው ? እነ አባ ዮናስ በ«አሮጊቷ ሣራ» አስተምህሮአቸው «ቤተክርስቲያኒቱ በ4ኛው ክፍለ ዘመን አባ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን ከሰበኩበት ጊዜ በኋላ ወንጌል አልተሰበከችም የወላድ መካን ሆና የኖረች ናት» በማለት አሁን እነርሱ ያንን ለመፈጸም የተወለዱ አድርገው አቅርበዋል፡፡ የእነዚህ ሰባክያን የ«አሮጊቷ ሣራ» አስተምህሮስ ከዚህ አንጻር ምን ይላል ?
ይህ ብቻ ሳይሆን አባ ዮናስ «ይህ ትውልድ የኢያሪኮን ግንብ ያፈርሳል» ያለው ቤተ ክርስቲያኒቱን ዒላማ ያደረገ ፉከራው በእነዚህ ሰባክያን የመዝሙር መንደርደሪያዎች ውስጥ ከሚነገረውና «መዶሻ ያልያዘ ሠራዊት ኢያሪኮን ያፈርሳል…» ከሚሉት አዝማች ቃል ጋር ያለውንም የትርጉም ዝምድና መጤን እንዳለበት እንድናስብ ያስገድዳል፡፡ በተመሳሳይ ይህንኑ መንገድ ተከትሎ በየደረጃው ምእመናን እነ አባ ዮናስ በግልጽ ያወጁት የ«ተሐድሶ» ፕሮቴስታንታዊ አስተምህሮ ዓውደ ምህረቶቻችን ላይ አሁንም ወደቆሙ «መምህራን» መሻገር አለመሻገሩን ቃሎቻቸውን እያጠኑ ለመመርመር ተገደዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን የሚመለከታቸው አካላትም የእነዚህን «ሰባኪያን» ትምህርት መርምረው ካለማወቅ በስሕተት የቀረበ ትምህርት መሆኑን ወይም በድፍረት የቀረበ ለ«ተሐድሶ» ዘመቻ የጥፋት ፈትል ማጠንጠኛ መሆን አለመሆኑን ለይተው እንደሚያቀርቡ ተስፋ እናደርጋለን፡፡
ምንጭ፦ ሐመር 19ኛ ዓመት ቁጥር 2