ሰሙነ ሕማማት(ዘረቡዕ)

በመምህር ኃይለማርያም ላቀው

 

በቅዱስ ማቴዎስና በቅዱስ ማርቆስ አዘጋገብ መሠረት ሦስት ነገሮች በዕለተ ረቡዕ ተደርገዋል፤ እነርሱም የሚከተሉት ናቸው፡፡

1.    የካህናት አለቆች÷ የሕዝብ ሽማግሌዎችና ጸሐፍት ፈሪሳውያን በጌታችን ላይ  ተማክረዋል፤

2.    ጌታችን በስምዖን ዘለምጽ ቤት ሳለ አንዲት የተጸጸተች ሴት ሽቱ ቀብታዋለች፡፡

3.    ከዳተኛው ይሁዳ ጌታችንን አሳልፎ ለመስጠት ከጸሐፍት ፈሪሳውያንና ከካህናት አለቆች ዘንድ 30 ብር ተመዝኖለታል፡፡

የካህናት አለቆችና የሕዝብ ሹማምንት በጌታችን ላይ ይሙት በቃ ለመወሰን የሰበሰቡት ሸንጐ “ሲኒሃ ድርየም” ይባላል፡፡ በዚህ ሸንጐ ላይ በአብዛኛው የተሰየሙት ሰዱቃውያን ሲሆኑ የተቀሩቱ ደግሞ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ነበሩ፡፡ ሸንጐው በአጠቃላይ 72 አባላት የነበሩት ሲሆን የሚመራው በሊቀ ካህናቱ ቀያፋ ነበር፡፡

 

በዕለቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እንዴት ይዘው እንደ ሚገድሉት መክረዋል፡፡ ከዳተኛው ይሁዳ በጸሐፍት ፈሪሳውያንና በካህናት አለቆች ዘንድ ይጉላላ የነበረውን ጥላቻ ያውቁ ስለነበር “ምን ልትሰጡኝ ትወዳላችሁ እኔም አሳልፌ እሰጣችኋለሁ” በማለት ጌታችን አሳልፎ ሊሰጣቸው እንደሚችል ተዋውሏል፡፡ የአስቆሮቱ ይሁዳ ጌታችን ያስተምር በነበረበት ወቅት ከተለያዩ ሰዎች የሚገባውን ገንዘብ ሰብሳቢ /ዐቃቤ ንዋይ/ ነበር፡፡ ከሚሰበሰበው ሙዳየ ምጽዋት ለግል ጥቅሙ እየቀረጠ የማስቀረት የእጅ አመል ነበረበት፡፡ ይሁዳ ፍቅረ ንዋይ እንደሚያጠቃው ድብቅ አመሉ ጎልቶ የወጣው ጌታችን በለምጻሙ በስምዖን ቤት ሳለ አንዲት ሴት ዋጋው ውድ የሆነ ሽቱ በቀባችው ጊዜ ይሁዳ የተቃውሞ ድምፅ ካሰሙት አንዱ ነበር፡፡  “ይህ ሽቱ ተሽጦ ለድሆች ቢሰጥ መልካም ነበር” በማለት ያቀረበው ሐሳብ “አዛኝ መሳይ ቅቤ አንጓች” እንደ ሚባለው ነበር፡፡ ሽቱ ሲሸጥ የሚያገኘው ጥቅም አለ፤ ሽቶ ከፈሰሰ የሚተርፈው የለም፡፡ ይህ በመሆኑ ተቆርቋሪ መስሎ ያቀረበው ሐሳብ ተቀባይነት ስላጣ ማኩረፊያ ያገኘ መስሎት በቀጥታ ከካህናት አለቆች ዘንድ ሄዶ ተዋዋለ፡፡ ብር 30 ተመዘነለት፡፡ ይህ አሳዛኝ ታሪክ በሦስቱ ወንጌላት ውስጥ በሚከተሉት ጥቅሶች ቀጽፎ እናገኛለን፡፡ ማቴ.26÷3-16፤ ማር.14÷1-11፤ ሉቃ.22÷1-6 ይመልከቱ፡፡

 

የአስቆሮቱ ይሁዳ እንደ ሌሎች ሐዋርያት ከጌታችን እግር ስር ተምሯል፡፡ በረከተ ኅብስቱን ተመግቧል፡፡ የተለያዩ ገቢረ ተአምራት በጌታችን እጅ ሲደረጉ ሁሉ ተመልክቷል፡፡ ጌታችንም ከሌሎቹ ሁሉ ሳይለየው እግሩን አጥቦታል፤ ከዳተኛው ይሁዳ ግን ለሐዋርያነት የጠራውን ተንበርክኮ እግሩን ያጠበውን ጌታውን አሳልፎ ሰጥቷል፡፡ “የሰው ልጅስ ስለ እርሱ እንደ ተጻፈ ይሄዳል÷ ነገር ግን የሰው ልጅ አልፎ ለሚሰጥበት ለዚያ ሰው ወዮለት እንደ ተባለ፡፡” ማቴ.26÷24፡፡ ሌሎች ሐዋርያት ከጌታችን ዘንድ ፍቅሩን ገንዘብ ሲያደርጉ ይሁዳ ግን እርግማንን ነው ያተረፈው፡፡ “ገንዘብ የኃጢአት ስር ነው” ተብሎ አንደ ተነገረ ይህ የኃጢአት ስር የክርስቲያኖችን ሕይወት ሊያደርቅ ስለሚችል ለገንዘብ ያለን ፍቅር በልኩ ሊሆን ይገባል፡፡ ሰው ይህን ህልም ቢያተርፍ ነፍሱን ከጐዳ ምን ይጠቅመዋል ተብሎ የተነገረውን ቃል ልብ ማለት ጠቃሚ ነው፡፡

 

ክርስቲያን ነን በማለት የክርስትናውን ስም በመያዝ እምነታቸውን፣ የቆሙበትን ዓላማ በመገንዘብ የሚለውጡ ሰዎች ዛሬም እንደ ይሁዳ ጌታችንን እየሸጡት እንደሆነ ሊገነዘቡ ይገባል፡፡ ለድሆች መመጽወት ክርስቲያናዊ ግዴታ ነው፡፡ ዳሩ ግን በድሆች ስም የሰውን ገንዘብ ለግል ጥቅም ማዋል እጅግ የከፋ ኃጢአት ነው፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰዎች ለገንዘብ ብለው ድሆችን ለረሃብ ለችግር ባልንጀራቸውን ለመከራ እና ለሞት አሳልፈው ሲሰጡ ምንም አይጸጽታቸውም፡፡ እውነተኛ ክርስቲያኖች ግን ሕይወታችንን ለገንዘብ ፍቅር ሳይሆን ለእምነታችንና ለባልንጀራችን አሳልፈን መስጠት ይኖርብናል፡፡ በፍቅረ ንዋይ ተጠምደን ሰዎችን አሳልፎ በመስጠት ለአይሁዳዊ ሸንጐ ምቹ ሆነን መገኘት እንደሌለብን መገንዘብ አለብን፡፡