commitiee

30ኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ተጀመረ

{gallery count=1 width=350 height=300 counter=1 links=0 alignment=center animation=3000}smg30{/gallery}

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን 30ኛው መደበኛ መንፈሳዊ ጉባኤ ጥቅምት 7 ቀን 2004 ዓ.ም በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ከጠዋቱ 3 ሰዓት በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ጸሎተ ቡራኬ ተጀምሯል፡፡

 

የ48ቱ አህጉረ ስብከት ሊቃነ ጳጳሳት በከፊል የተገኙ ሲሆን ሁሉም የሀገር ውስጥ ሥራ አስኪያጆች ፣የመንበረ ፓትሪያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያ ሓላፊዎች ፣በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር የሚገኙ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች ፣ በኢትዮጵያ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ፣ የሕፃናትና ቤተሰብ ጉዳይ ድርጅት፣ የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ሓላፊዎች የጉባኤው ተሳታፊዎች ናቸው።

የመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ካህናት “ስምዐነ አምላክነ ወመድኃኒነ ተስፋሆሙ ለኩሎሙ አጽናፈ ምድር” የሚለው የዳዊት መዝሙር ተሰብኮ “በምድር የምታስሩት በሰማይ የታሰረ ይሆናል በምድርም የምትፈቱት በሰማይ የተፈታ ይሆናል፡፡…. ሁለት ወይም ሦስት በስሜ በሚሰበሰቡበት በዚያ በመካከላቸው እሆናለሁና” የሚለው የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 18 ቁጥር 18 በቅዱስነታቸው ተነቧል፡፡

 

ቅዱስነታቸው በጸሎተ ወንጌል ጉባኤውን ባርከው ከከፈቱ በኋላ በሰጡት ቃለ ምእዳን ሰው መግባባት የሚችለው እግዚአብሔር በሰጠው አእምሮ ሲጠቀምበትና በፈሪሃ እግዚአብሔር ሲኖር ነው። ፈሪሃ እግዚአብሔር ካለ ሰላም፣ ፍቅር፣ መግባባት፣ መዋደድና መከባበር ይኖራል ብለው በሰላማዊ መንገድ ሓላፊነትን መወጣት እንዲገባ አሳስበዋል፡፡

ቅዱስ ፓትርያርኩ አያይዘው በ2003 ዓ.ም በሞት የተለዩንን ብፁዕ አቡነ በርናባስን፣ ብፁዕ አቡነ ይስሐቅንና ብፁዕ አቡነ ሚካኤልን በጸሎት እናስባቸው ብለው ጸሎት አድርሰዋል፡፡

 

ሊቀትጉሃን ኃይለ ጊዮርጊስ ዳኜ፣ መጋቤ ሰናያት አሰፋ ስዩም፣ ሊቀ ስዩማን ራደ አስረስ፣ ንቡረ እድ ተስፋዬ ተወልደና መጋቤ ሐዲስ ይልማ ቸርነት የአቋም መግለጫ ረቂቅ እንዲያዘጋጁ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ ለጉባኤው አቅርበው ጉባኤው የተመረጡትን አርቃቂዎች በሙሉ ድምጽ አሳልፈዋል፡፡commitiee

 

ከረፋዱ 4 ሰዓት ጀምሮ ለ45 ደቂቃ ያህል የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት አጠቃላይ ሪፓርት በብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የጠቅላይ ቤተ ክርህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የኢሉባቡርና ጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና በንቡረ እድ ኤልያስ አብርሃ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ ቀርቧል፡፡ ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሪፖርት ቀጥሎ የትግራይ ማዕከላዊ ዞን /አክሱም/ ሀገረ ስብከት ሪፖርት መቅረብ የነበረበት ቢሆንም የጋምቤላ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ለሌላ ተልእኮ ወደ ሱዳን ሀገረ ስብከት መሔድ እንዲችሉ ፈቃድ ጠይቀው ቅድሚያ ሪፖርታቸውን አቅርበዋል፡፡

 

በጠዋቱ መርሃ ግብር የትግራይ ማዕከላዊ ዞን፣ የሲዳማ፣ የሰሜን ጎንደር፣ የምሥራቅ ሀረርጌ፣ ሀገረ ስብከት ሪፖርት ቀርቧል፡፡ ከሰዓት በኋላ በተያዘው መርሃ ግብር ከቀኑ 8 ሰዓት እስከ 11፡30 ድረስ የጅማ ዞን ሀገረ ስብከት፣ በትግራይ ክልል ሀገረ ስብከት የመቀሌ፣ የኢሊባቡር፣ የድሬዳዋ፣ የጋሞጎፋ፣ የሰሜን ወሎ፣ የባሌ፣ የደቡብ ጎንደርና የምሥራቅ ወለጋ አህጉረ ስብከት ሪፖርት ቀርቧል፡፡

 

ረቡዕ ጥቅምት 8 ቀን 2004 ዓ.ም ከጠዋቱ 3 እስከ 6፡30 በነበረው መርሐ ግብር የአርሲ፣ የትግራይ ምሥራቅ /አዲግራት/፣ የምዕራብ ጎጀም፣ የከፋ ቦንጋ፣ የሰሜን ሸዋ፣ የአሶሳና የደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ሪፖርት ቀርቦ እንዳበቃ የቆሜ አቋቋም ሊቃውንት ወረብ አቅርበዋል፡፡

 

በሊቃውንቱ የቀረበው ወረብ እንደተጠናቀቀ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ፣ የምሥራቅ ጎጃም፣ የምዕራብ ሐረርጌና የትግራይ ደቡባዊ ዞን /ማይጨው/ አህጉረ ስብከት ሪፖርት በንባብ ተሰምቷል፡፡

 

ከሰዓት በኋላ በተያዘው መርሃ ግብር የደቡብ ኦሞ፣ የሰሜን ምዕራብ ሸዋ የሰላሌ ሀገረ ስብከት የሐዲያና ስልጤ፣ የዋግ ሕምራ፣ የምዕራብ ሸዋ፣ የአፋር፣ የአዊ ዞን፣ የሶማሊያ፣ የምዕራብ ወለጋ፣ የትግራይ ሰሜናዊ ምዕራብ ዞን ሽሬ ሀገረ ስብከትና የትግራይ ሰሜናዊ ምዕራብ ዞን ሽሬ ሀገረ ስብከትና የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሪፖርት ከቀረበ በኋላ ውይይት ተካሒዷል፡፡

 

30 ዓመት ያስቆጠረው የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ካሳለፈው ረዥም ጉዞ ጋር ሲነጻጸር የሚጠበቅበትን ውጤት እያስመዘገበ እንዳልሆነ በመንበረ ፖትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት የቀረበው ሪፓርት ያስረዳል፡፡

 

አጠቃላይ ጉባኤው እስከ ጥቅምት 11 ቀን 2004 ዓ.ም የሚቀጥል ሲሆን ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅሙ ውይይቶችና የውሳኔ ሐሳቦች እንደሚቀርቡበት ይጠበቃል፡፡