Entries by Mahibere Kidusan

ቅዱስ ሩፋኤል

የሰው ልጆች ከተያዙበት የኀጢአት ቍስል ይፈወሱ ዘንድ በአማላጅነቱና በጸሎቱ የማይለይ መልአክ ነው፡፡ ‹‹በበሽታ ዅሉ ላይ በሰው ልጆችም ቍስል ላይ የተሾመው ቅዱስ ሩፋኤል ነው›› በማለት ሄኖክ ከእግዚአብሔር መልአክ ያገኘውን የምስክርነት ቃል ጽፏል (ሄኖክ ፲፥፲፫)፡፡ ቅዱስ ሩፋኤል በሰውነታችን ላይ የሚወጣውን ደዌም ኾነ ቍስል ይፈውስ ዘንድ ከልዑል እግዚአብሔር ሥልጣን ተሰጥቶታል፡፡ ‹‹በሰው ቍስል ላይ የተሾመ ከከበሩ መላእክት አንዱ ቅዱስ ሩፋኤል ነው›› እንዳለ ሄኖክ (ሄኖክ ፮፥፫)፡፡ ለቈሰሉ ፈውስን የሚያሰጣቸው፤ ላረገዙ ሴቶች ረዳታቸው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ ሴት በፀነሰችበት ወቅት ቅዱስ ሩፋኤል አይለያትም፡፡ ሕፃኑ (ኗ በማኅፀን እያለ (ች) ተሥዕሎተ መልክዕ (በሥላሴ አርአያ መልኩ /ኳ/ መሳል) ከጀመረበት ቀን አንሥቶ እስከሚወለድበት ቀን ድረስ ቅዱስ ሩፋኤል በጥበቃው አይለያቸውም፡፡ በመውለጃቸው ቀን ሴቶች ከሚደርስባቸው ጭንቀትና ሕመም ስሙን ጠርተው ይማጸኑታል፡፡ ፈታሔ ማኅፀን ነውና ቅዱስ ሩፋኤልም ጭንቀታቸውን ያቀልላቸዋል፡፡

የ፳፻፲ ዓ.ም ዘመን መለወጫን አስመልክቶ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ የሰጡት ቃለ በረከት

የብርሃን ጸጋ ለሰው ልጆች ወይም በአጠቃላይ ለፍጥረታት ዅሉ ከተሰጠው የእግዚአብሔር ስጦታዎች ትልቁ ነው፤ ብርሃን የሥራ መሣሪያ ነው፤ ብርሃን የመልካም ነገር ሁሉ ተምሳሌት ነው፡፡ እግዚአብሔር ራሱ በባሕርዩ ብርሃን ከመኾኑም ሌላ በእርሱ ዘንድ የማይጠፋ ብርሃን እንዳለ በቅዱስ መጽሐፍ ተገልጿል፡፡ የሰው ልጅ ከወዲያ ወዲህ፣ ከወዲህ ወዲያ ተንቀሳቅሶ፣ ነግዶ፣ አርሶ፣ ሠርቶ፣ ተምሮና አስተምሮ ለኑሮው የሚያስፈልገውን ዅሉ ለማግኘት ብርሃን የግድ ያስፈልጋል፡፡

ዘመነ ክረምት – ክፍል ሰባት

ሕዝበ ክርስቲያኑም ለአዲሱ ዓመት ብቻ ሳይኾን ‹‹ለቅዱስ ዮሐንስ በዓል እንኳን በሰላም አደረሳችሁ›› እያሉ መልካም ምኞታቸውን ለወዳጅ ዘመዶቻቸው መግለጻቸው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት የቅዱስ ዮሐንስ በዓል ከአዲስ ዓመት መባቻ ጋር በአንድነት ሲከበር ለመቆየቱ ማስረጃ ነው፡፡ ይኸውም የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ከጳጕሜን ፩ ቀን ጀምሮ በእስር ቤት ከቆየ በኋላ መስከረም ፪ ቀን በሰማዕትነት ዐርፏል፡፡ ቅዱሱ የሐዲስ ኪዳን አብሣሪ ነውና፣ ደግሞም ዕለቱ ቃል ኪዳን የተቀበለበት ቀን ነውና ስሙና ግብሩ ከዘመን መለወጫ ጋር አብሮ ይታወስ ዘንድ በዓሉ መስከረም ፩ ቀን በሥርዓተ ማኅሌት ይከበራል፡፡ ለዚህም ነው – ሊቃውንቱ ‹‹ርእሰ ዐውደ ዓመት ዮሐንስ ወላዴ መጥቅዕ ወአበቅቴ›› እያሉ የአዲስ ዓመት መጀመርያ፣ የመጥቅዕ እና አበቅቴ መነሻ መኾኑን በሚገልጽ ኃይለ ቃል ቅዱስ ዮሐንስን የሚያወድሱት፡፡

ወርኀ ጳጕሜን

ጳጕሜን 5 ቀን በቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ዘንድ ‹ዕለተ ምርያ› ወይም ‹የተመረጠች ቀን› ትባላለች፡፡ ሊቃውንቱ የጌታችንን ልደት ሲያሰሉባት የቆየችው ዕለት በመኾኗ ነው ይህንን ስያሜ ያገኘችው፡፡ የጌታችንን ልደት ቀን የምትወስነው የጳጕሜን 5ኛዋ ቀን ናት፡፡ በዓለ ልደት የሚውለውም ጳጕሜን 5 በዋለበት ቀን ነው፡፡ ለምሳሌ ዘንድሮ (2009 ዓ.ም) ጳጕሜን 5 ቀን እሑድ ይውላል፤ ስለዚህም በ2010 ዓ.ም የሚበረው በዓለ ልደት እሑድ ይኾናል ማለት ነው፡፡ በየአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ ጳጕሜን 6 ቀን ስትኾን ልደት በ28 የሚከበረውም በዓለ ልደት ጳጕሜን 5 ቀንን (ዕለተ ምርያን) ስለማይለቅ ነው፡፡ በዘመነ ዮሐንስ ስድስተኛዋ የጳጕሜን ቀን በዓለ ልደትን በአንድ ቀን ዝቅ ብሎ እንዲከበር ስለምታደርገው ልደትን ታኅሣሥ 28 ቀን እናከብራለን፡፡ ታድያ ምነው ጥምቀት፣ ግዝረትና ሌሎችም በዓላት አይለወጡም? ቢሉ ሊቃውንቱ የሚሰጡት ምላሽ ‹‹ትውልድ ሱባዔ እየቈጠረ በተስፋ የጠበቃት ዕለተ ልደትን ስለ ኾነ ነው፡፡ ሌሎቹ በዓላት የመጡት በልደቱ ምክንያት ነውና›› የሚል ነው፡፡

ክረምት – ካለፈው የቀጠለ

በገበሬ የተመሰለው ኢየሱስ ክርስቶስም እኛ በዓለም ላይ ያለን የሰው ዘሮች በሙሉ በመከር ያፈራውም ያላፈራውም እንደሚሰበሰብ ያሳየናል፡፡ ‹‹እንግዲህ ወንድሞች ሆይ፣ ጌታ እስኪመጣ ድረስ እነሆ ገበሬው የፊተኛውን፣ የኋለኛውን ዝናም እርሱን የታገሠ የከበረውን የምድር ፍሬ ይጠብቃል፡፡ እናንተም ደግሞ ታገሡ፤›› እንዳለ ሐዋርያው (ያዕ. ፭፥፯-፱)፡፡ ገበሬ ቅጠሉ ፍሬ እስከሚሰጥ ምን ያህል መከራን እንደሚታገሥ እኛም መንግሥተ ሰማያት ለመግባት ቅጠል ብቻ የኾነ ማንነታችን የንስሐ ፍሬ እስኪያፈራ ድረስ መከራውን መታገሥ ይገባናል፡፡ ምድራዊ ፍሬ ለማግኘት ይህን ያህል መጠበቅና መታገሥ ካስፈለገ ሰማያዊ ዋጋ ለመቀበል ምን ያህል መታገሥ ያስፈልግ ይኾን? ከወርኃ ቅጠል ያለ ፍሬ ብንገኝ መርገምን እንደምናተርፍ፣ ብናፈራ ግን ገበሬ ምርቱን ደስ ብሎት እንዲሰበስብ ፈጣሪያችንም በእኛ እንደሚደሰትና ዋጋችንን እንደሚሰጠን እንማራለን፡፡ ክረምት ጥልቅ ትምህርት የምንማርበት እግዚአብሔር በሰፊው የሚገለጽበት ወቅት ነው፡፡

ክረምት – የመጀመርያ ክፍል

ውኃ መንፈሳዊ ምግብና (ምግብነት ወይም አገልግሎት) አለው፡፡ ደገኛዋ የሰው ልጆች ጥምቀት በውኃ መፈጸሟ የውኃ ጥቅም የጎላ መኾኑን ያሳየናል፡፡ የጥምቀታችን መሥራች ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአባቶቻችንና በእኛ ላይ የነበረውን የዕዳ ደብዳቤ ያጠፋልን በውኃ ተጠምቆ ነውና (ማቴ. ፫፥፲፫)፡፡ ‹‹ከውኃና ከመንፈስ ያልተወለደ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ዮሐ. ፫፥፭)፡፡ ይኸውም ውኃ ከሥጋዊ ምግብናው ባሻገር እኛ የእግዚአብሔር ልጆች የምንኾንበት ምሥጢር መፈጸሚያ መኾኑን ያስረዳል፡፡ በሌላ መልኩ ጌታችን የእኛን ሥጋ ለብሶ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተገልጾ ባስተማረ ጊዜ ‹‹እንጀራ ለመነ›› ሳይኾን ‹‹ውኃ ለመነ›› ተብሎ ነው የተነገረለት፡፡ ‹‹ውኃ አጠጪኝ አላት›› እንዲል (ዮሐ. ፬፥፯)፡፡ እስራኤልን ዐርባ ዓመት ውኃ ከጭንጫ እያፈለቀ ያጠጣ አምላክ ውኃ የለመነው ውኃ አጥቶ አይደለም፡፡ ውኃ ትልቅ ምሥጢር የሚፈጸምበት መኾኑን ለመግለጽ ነው እንጂ፡፡ ይኸውም ሊታወቅ ‹‹የእግዚአብሔርን ስጦታና ውኃ አጠጪኝ የሚልሽ ማን መኾኑን ብታውቂስ አንቺ ደግሞ በለመንሺው፤ እርሱም የሕይወትን ውኃ በሰጠሸ ነበር … እኔ ከምሰጠው ውኃ የሚጠጣ ለዘለዓለም አይጠማም፤›› በማለት አስተምሮአል፡፡

በአሜሪካ ለአራተኛ ጊዜ ዐውደ ርእይ ተካሔደ

በመርሐ ግብሩ ማጠቃለያ ዕለት ቃለ መጠይቅ የተደረገላቸው አንዳንድ ምእመናን በዐውደ ርእዩ በመሳተፋቸው ደስተኞች መኾናቸውን ገልጠው ማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎቱን በአገር ውስጥ ብቻ ሳይገድብ ከኢትዮጵያ ውጪ ለሚኖሩ ምእመናንም ትምህርተ ወንጌል እንዲዳረስ የሚያደርገውን ጥረት አድንቀዋል፡፡ ይህ የማኅበሩ አገልግሎት ተጠናክሮ ሊቀጥል፣ ዐውደ ርእዩም በመላው ዓለም ሊዳረስ እንደሚገባው አስተያየት ሰጪዎቹ አሳስበዋል፡፡

የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ዕረፍት

አቡነ ተክለ ሃይማኖት የዕረፍታቸው ጊዜ መቃረቡን ባወቁ ጊዜ የመንፈስ ልጆቻቸውን ጠርተው ጌታችን የነገራቸውን ዅሉ አስረድተው አባታዊ ምክርና ተግሣፅ ከሰጧቸው በኋላ ነሐሴ ፳፬ ቀን ከዚህ ዓለም ድካም ዐርፈዋል፡፡ የመንፈስ ልጆቻቸውም ለአንድ ቅዱስ አባትና ካህን በሚገባ ሥርዓት በማኅሌት፣ በዝማሬና በምስጋና ቀብረዋቸዋል፡፡ ጌታችንም ከእመቤታችንና ከቅዱሳን መላእክት ጋር ተገልጾላቸዋል፤ ነፍሳቸውንም ‹‹የጠራሽ፣ ንጽሕት ነፍስ ሆይ ወደ እኔ ነዪ›› ብሎ በክብር ተቀብሏታል፡፡ በመጽሐፈ ገድላቸው እንደ ተጠቀሰው አቡነ ተክለ ሃይማኖት በዚህ ዓለም የኖሩበት ዕድሜ ዘጠና ዘጠኝ ዓመት ከዐሥር ወር ከዐሥር ቀን ነው፡፡ በእናት አባታቸው ቤት ፳፪ ዓመት፤ በከተታ ፫ ዓመት፤ በይፋት ፱ ወር፤ በዳሞት ፲፪ ዓመት፤ በአማራ ፲ ዓመት፤ በሐይቅ ፲ ዓመት፤ በደብረ ዳሞ ፲፪ ዓመት፤ በትግራይና በኢየሩሳሌም ገዳማት ፩ ዓመት፤ ዳዳ በሚባል አገር ፩ ወር፤ በደብረ አስቦ ገዳም ፳፱ ዓመት ከ፲ ቀን መቆየታቸውን መጽሐፈ ገድላቸው ይናገራል (ገ.ተ.ሃ ፶፱፥፲፬-፲፭)፡፡

ዘመነ ክረምት – ክፍል ስድስት

ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን፣ መዓልት የሚባለው ክፍለ ክረምት ‹‹ቡሄ ካለፈ የለም ክረምት፤ ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት›› እንደሚባለው ክረምቱ እየቀለለ፣ ማዕበሉ እየቀነሰ፣ ዝናሙ እያባራ፣ ሰማዩ እየጠራ የሚሔድበት የንጋት፣ የወጋገን፣ የብርሃን ጊዜ ነው፡፡ ልክ እንደ ዘመኑ እኛም እንደ ደመና በልባችን የቋጠርነውን ቂምና በቀል፤ እንደ ጨለማ በአእምሯችን የሣልነውን ክፋትና ኑፋቄ ወይም ክህደት፤ እንደ ዝናምና ማዕበል በወገን ላይ ያደረስነውን ጥፋትና በደል በንስሐ ፀሐይ አስወግደን ወደ ብርሃኑ ሕገ እግዚአብሔር፤ ወደ ብርሃኑ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ፤ ወደ ብርሃኑ ምግባረ ሠናይ፤ ወደ ብርሃኑ ክርስትና እንመለስ፡፡ እንዲህ እንድናደርግም ልዑል እግዚአብሔር ‹‹በሕይወታችሁ ውስጥ ብርሃን ይኹን!›› ይበለን፡፡ እርሱ ‹‹ብርሃን ይኹን›› ካለ የኀጢአት ጨለማ በእኛ ላይ ለመሠልጠን የሚችልበት ዓቅም አያገኝምና፡፡

ዐውደ ርእዩ በኢንድያናፖሊስ ከተማ ቀረበ

እንደ ማእከሉ ማብራሪያ የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ፣ ሐዋርያዊ አገልግሎቷ፣ ተጋድሎዋ፣ ያጋጠሟት ችግሮች እና ችግሮቿን ከመፍታት አንጻር የምእመናን ድርሻ እንደዚሁም የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት በቤተ ክርስቲያን የሚሉ ጉዳዮች በዐውደ ርእዩ የተካተቱ የትዕይንት ክፍሎች ሲኾኑ፣ ትዕይንቶቹም በአማርኛ፣ ትግርኛ እና እንግሊዝኛ ቋንቋዎች ተተርጕመው ለወጣቶች እና ሕፃናት በሚመጥን መልኩ ቀርበዋል፡፡