የድንግል ማርያም ክብሯ፣ ዕረፍቷ እና ትንሣኤዋ
እመቤታችን ልጇን ይዛ ከአገር አገር በረሀብና ጥም የተንከራተተችበት ጊዜ አሁን አለፈ፡፡ ታናሽ ብላቴና ሳለች ልጇን አዝላ በግብጽ በረኀ የተቀበለችው መከራ ዅሉ ፍጻሜ አገኘ፡፡ ከእግረ መስቀል ሥር ወድቃ የልጇን የቆሰለ ገላ እየተመለከተች የደረሰባት ልብ የሚሰነጥቅ ሐዘን ወደ ደስታ ተለወጠ፡፡ ‹‹በነፍሷ ሰይፍ ያልፋል›› ተብሎ የተነገረው ልብ የሚሰነጥቅ መከራ እንደ ነቢዩ ቃለ ትንቢት የሚቀጥልበት ጊዜ ተፈጸመ፡፡ እርሷ ባለችበት ሥፍራ የሕይወት ትንሣኤ ያላቸው ሰዎች ይኾኑ ዘንድ አስቀድማ ከሙታን ተለይታ በመነሣት የተጠበቀልን ተስፋ ማሳያ ኾነችን፡፡ በእግዚአብሔር መንግሥት ስደት፣ መከራ፣ ሐዘን፣ ሰቆቃ የለም፤ መገፋት መግፋትም የለም፡፡ ከእንግዲህ ወዲያ ልጇ ሲንገላታ፣ ሲሰደድ ሲገረፍ፣ ሲሰቀል፣ ሲቸነከር ያየችበት ዓለም አለፈ፡፡ አሁን የልጇን ልዕልና ከሚያደንቁ ጋር ታደንቃለች፤ ከፍ ከፍ ከሚያደርጉት ጋር ታከብረዋለች፡፡ ይኸውም ከገቡ የማይወጡበት፤ ሐዘን፣ መከራ፣ ችግር የሌለበት ሰማያዊት አገር ነው፡፡ ቅዱሳን ሩጫቸውን ጨርሰው የድል አክሊልን የሚቀዳጁበት ሥፍራ ነው፡፡ በዚያም ከፍጡራን ዅሉ ከፍ ባለ በታላቅ ክብርና ጸጋ ለዘላለም ትኖራለች፡፡