Entries by Mahibere Kidusan

የድንግል ማርያም ክብሯ፣ ዕረፍቷ እና ትንሣኤዋ

እመቤታችን ልጇን ይዛ ከአገር አገር በረሀብና ጥም የተንከራተተችበት ጊዜ አሁን አለፈ፡፡ ታናሽ ብላቴና ሳለች ልጇን አዝላ በግብጽ በረኀ የተቀበለችው መከራ ዅሉ ፍጻሜ አገኘ፡፡ ከእግረ መስቀል ሥር ወድቃ የልጇን የቆሰለ ገላ እየተመለከተች የደረሰባት ልብ የሚሰነጥቅ ሐዘን ወደ ደስታ ተለወጠ፡፡ ‹‹በነፍሷ ሰይፍ ያልፋል›› ተብሎ የተነገረው ልብ የሚሰነጥቅ መከራ እንደ ነቢዩ ቃለ ትንቢት የሚቀጥልበት ጊዜ ተፈጸመ፡፡ እርሷ ባለችበት ሥፍራ የሕይወት ትንሣኤ ያላቸው ሰዎች ይኾኑ ዘንድ አስቀድማ ከሙታን ተለይታ በመነሣት የተጠበቀልን ተስፋ ማሳያ ኾነችን፡፡ በእግዚአብሔር መንግሥት ስደት፣ መከራ፣ ሐዘን፣ ሰቆቃ የለም፤ መገፋት መግፋትም የለም፡፡ ከእንግዲህ ወዲያ ልጇ ሲንገላታ፣ ሲሰደድ ሲገረፍ፣ ሲሰቀል፣ ሲቸነከር ያየችበት ዓለም አለፈ፡፡ አሁን የልጇን ልዕልና ከሚያደንቁ ጋር ታደንቃለች፤ ከፍ ከፍ ከሚያደርጉት ጋር ታከብረዋለች፡፡ ይኸውም ከገቡ የማይወጡበት፤ ሐዘን፣ መከራ፣ ችግር የሌለበት ሰማያዊት አገር ነው፡፡ ቅዱሳን ሩጫቸውን ጨርሰው የድል አክሊልን የሚቀዳጁበት ሥፍራ ነው፡፡ በዚያም ከፍጡራን ዅሉ ከፍ ባለ በታላቅ ክብርና ጸጋ ለዘላለም ትኖራለች፡፡

‹‹አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፤ አንተና የመቅደስህ ታቦትም›› (መዝ. ፻፴፩፥፰)

እንደዚህ ያለውን ትንሣኤ ከእርሷ በቀር ሌሎች ቅዱሳን ወይም ነቢያትና ሐዋርያት አላገኙትም፡፡ በዚህም ኹኔታ የቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ ከማናቸውም ትንሣኤ ልዩ ኾኖ እናገኘዋለን፡፡ ይህም ትንሣኤ ዘለዓለማዊ፣ ከዳግም ሞተ ሥጋ ነጻ የኾነ ትንሣኤ ነው፡፡ ዕርገቷም በመጽሐፍ ቅዱስ ከተገለጸው ከእነ ሄኖክና ኤልያስ ዕርገት የተለየ ነው፡፡ «ሄኖክ ሞትን እንዳያይ በእምነት ተወሰደ፤ እግዚአብሔርም ስለ ወሰደው አልተገኘም» ተብሎ እንደ ተጸፈ (ዕብ. ፲፩፥፭)፣ ሄኖክ ወደ ሰማይ ያረገው በምድር ሳለ እግዚአብሔርን በእምነቱና በመልካም ሥራው ስላስደስተና በሥራውም ቅዱስ ኾኖ ስለ ተገኘ ነው፡፡ ኾኖም ግን ወደፊትም ገና ሞት ይጠብቀዋል፤ ሞቶም ትንሣኤ ዘጉባኤ ያስፈልገዋል፡፡ ነቢዩ ኤልያስም በእሳት ሠረገላም ቢነጠቅም (፪ኛ ነገ. ፪፥፲) ወደፊት ሞት ይጠብቀዋል፤ ትንሣኤ ዘጉባኤም ያስፈልገዋል፡፡ የእመቤታችን ትንሣኤ ግን ሞት የሌለበት ዘለዓለማዊ ትንሣኤ ነው፡፡

እግዚአብሔር በደብረ ታቦር

አንድም ደብረ ታቦር የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክነቱንም ሰዉነቱንም በደብረ ታቦር እንደ ገለጠ ከእመቤታችን ከነፍስና ከሥጋዋ ጋር ተዋሕዶ ሰዉም አምላካም መኾኑን አሳይቷል፡፡ አምላክ ሰው፤ ሰውም አምላክ መኾኑ በድንግል ማርያም ማኅፀን ተገለጧል፡፡ በደብረ ታቦር ነቢያትም ሐዋርያትም እንደ ተገኙ እመቤታችንም የነቢያት ትንቢት ተፈጽሞባታል፤ የሐዋርያት ስብከት ጸንቶባታል፡፡ እርሷ አምላክን ለመሸከም ተመርጣለችና እመቤታችን በደብረ ታቦር ትመሰላለች፡፡ እንደዚሁም ደብረ ታቦር የአብያተ ጉባኤ (የአብነት ትምህርት ቤቶች) ምሳሌ ነው፡፡ በደብረ ታቦር የእግዚአብሔር ሦስትነት፣ አንድነት እንደ ታወቀ፤ ብርሃነ መለኮቱም እንደ ተገለጠ፤ ነቢያትና ሐዋርያትም እንደ ተገኙ ዅሉ በየአብነት ትምህርት ቤቶችም ምሥጢረ ሥላሴ፣ ነገረ መለኮት፣ ክብረ ቅዱሳን፣ ትንቢተ ነቢያትና ቃለ ወንጌል ዘወትር ይነገራል፣ ይሰበካል፤ ይተረጐማል፡፡

በዓለ ደብረ ታቦር እና ቡሄ

ወላጆች ለልጆቻቸው የበዓለ ደብረ ታቦርን መንፈሳዊነት፣ የመዝሙሮቹን ያሬዳዊነትና አከባበሩን ከቤተ ክርስቲያን መምህራን በመጠየቅ ማስተማር፤ ልጆችም ከወላጆች ወይም ከመምህራን በመጠየቅ የበዓሉን አከባበር መረዳትና የዚህን በዓል መንፈሳዊ ትውፊት ሳይበረዝ ለትውልድ ማስተላለፍ ይገባቸዋል፡፡ ‹‹ድምፅህን ሰማና በብሩህ ደመና፤ የቡሄው ብርሃን ለእኛ በራልን …›› የሚለውንና ይህን የሚመስሉ መንፈሳውያን መዝሙራትን እየዘመሩ በየቤቱ በመዘዋወር የሚያገኙትን ዳቦና ገንዘብ ለነዳያንና ለቤተ ክርስቲያን የሚሰጡ ልጆችንም ማበረታታትና አርአያነታቸውን መከተል ይኖርብናል፡፡

ደብረ ታቦር አምሳለ ቤተ ክርስቲያን – ካለፈው የቀጠለ

ምሥጢር ይገለጥልን ባላችሁ ጊዜ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገስግሱ፤ ቤተ ክርስቲያንን ደጅ ጽኑ ለማለት ጌታችን ምሥጢሩን በተራራ ገለጠ፡፡ ወደ ተራራው ሲወጣም ስምንቱን ደቀ መዛሙርቱን ከይሁዳ ጋር ከተራራ እግር ሥር ትቶ ሦስቱን አስከትሎ ወጥቷል፡፡ ለሦስቱ በተራራው ላይ የተገለጠው ድንቅ ምሥጢርም ከእግረ ደብር ላሉት በሳምንቱ ተገልጧል፤ ከይሁዳ በቀር፡፡ ለዚህ ምሥጢር ብቁ ያልነበረው ይሁዳ ብቻ ነው፡፡ ይህም ተገቢውን ምሥጢር ለተገቢው ሰው መንገር እንደሚገባ፤ ለማይገባው ደግሞ ከመንገር መቆጠብ ተገቢ እንደ ኾነ ያስተምረናል፡፡ ‹‹እመኒ ክዱን ትምህርትነ ክዱን ውእቱ ለሕርቱማን ወለንፉቃን …፤ ወንጌላችን የተሰወረ ቢኾንም እንኳን የተሰወረባቸው ለሚጠፉት ነው፡፡ እግዚአብሔርን የሚመስለው የክርስቶስ የክብሩ ወንጌል ብርሃን እንዳያበራላቸው የዚህ ዓለም አምላክ ልባቸውን አሳውሯልና፤›› (፪ኛ ቆሮ. ፬፥፫-፭) በማለት ሐዋርያው የሰጠው ትምህርትም ይህን መሰል ምሥጢር ለሚገባው እንጂ ለማይገባው ሰው መግለጥ ተገቢ አለመኾኑን የሚያስረዳ ነው፡፡

ደብረ ታቦር አምሳለ ቤተ ክርስቲያን – የመጀመርያ ክፍል

ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን ለደቀ መዛሙርቱ የገለጠበት፤ ነቢያት ሊያዩት የተመኙትን ያዩበት ነቢያትና ሐዋርያት በአንድነት የተገናኙበት፤ ተገናኝተውም እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ኾነው የክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት የመሰከሩበት፤ እግዚአብሔር ወልድ በክበበ ትስብእትና በግርማ መለኮት የተገለጠበት፤ እግዚአብሔር አብ በደመና ‹‹የምወደው፣ ለተዋሕዶ የመረጥኩት በእርሱ ህልው ኾኜ የምመለክበት ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት፤›› ብሎ የመሰከረበት፤ መንፈስ ቅዱስም በአምሳለ ርግብ የወረደበት፤ እግዚአብሔር አንድነቱን፣ ሦስትነቱን የገለጠበት እነ ቅዱስ ጴጥሮስ ለመኖር የተመኙት ደብረ ታቦር ነው፡፡ በዓሉ የጌታችን ሲኾን በስሙ ደብረ ታቦር ተብሏል፡፡ ይህ በዓል ያን ጊዜ ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን አስከትሎ ወደ ተራራው ሲወጣ፣ በተራራው ራስ ላይ ምሥጢሩን ሲገልጥላቸው፣ አእምሮአቸውን ሲከፍትላቸው፣ ከግርማው የተነሣ ፈርተው ሲወድቁና ሲያነሣቸው በዐይነ ሕሊናችን የምንመለከትበት በዓል ነው፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን መደበኛ የቴሌቭዥን መርሐ ግብሩን ሊቀጥል ነው

በአሌፍ የቴሌቭዥን ጣቢያ በአዲስ ዓመት ልዩ ዝግጅት የሚጀምረው የማኅበሩ የቴሌቭዥን መርሐ ግብር በአማርኛ፣ በአፋን ኦሮሞ እና በትግርኛ ቋንቋዎች የሚቀርብ ሲኾን፣ ለጊዜው በየቀኑ ለሁለት ሰዓታት እንደሚተላለፍ የማኅበረ ቅዱሳን ጽ/ቤት አስታውቋል፡፡

የተራራው ምሥጢር (ማቴ. ፲፯፥፩-፱)

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጠብቃ ካቆየቻቸው መንፈሳውያት እሴቶች መካከል በጌታችን፣ በእመቤታችንና በቅዱሳኑ ስም በዓላትን ማክበር ይገኙበታል፡፡ ከእነዚህም አንዱ የደብረ ታቦር በዓል ነው፡፡ በዓሉ ዳቦ በመድፋት፣ ጠላ በመጥመቅ በየቤቱ በደማቅ ሥርዓት ይከበራል፡፡ በተለይ የአብነት ተማሪዎች ከሕዝቡ በመለመን ስሙን ይጠራሉ፡፡ ይህም ልንጠብቀው የሚገባን መንፈሳዊ እሴታችን ነው፡፡ ጌታችን የቅዱሳኑን መታሰቢያ በተመለከተ ሲናገር ‹‹በደቀ መዝሙር ስም ቀዝቃዛ ውኃ ያጠጣ ዋጋው አይጠፋበትም›› በማለት ተናግሯል (ማቴ. ፲፥፵፪)፡፡ በቅዱሳኑ ስም የሚደረግ ምጽዋት ይህን ያህል በረከት ካስገኘ፣ በራሱ በባለቤቱ ስም የሚደረገውማ እንደምን አብዝቶ ዋጋ አያሰጥ? ክርስቲያኖች! በአጠቃላይ ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠበትን ከጌታችን ዐበይት በዓላት አንዱ የኾነውን የደብረ ታቦርን በዓል የምናከብረው በዚህ መንፈስ ነው፡፡ አምላካችን ‹‹ለሚወዱኝ እስከ ሺሕ ትውልድ ድረስ ምሕረትን የማደርግ እኔ እግዚአብሔር ነኝ›› (ዘፀ. ፳፩፥፮) ብሏልና በዓሉን በክርስቲያናዊ ሥርዓት በማክበር የበረከቱ ተሳታፊዎች መኾን ይገባናል፡፡

የምሥጢር ቀን

እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ይህ ጸጋ በቤተ ክርስቲያን ሲታደል ይኖራል፡፡ ወንዶቹ በተወለዱ በዐርባ፤ ሴቶቹ ደግሞ በሰማንያ ቀናቸው ወደ ቤተ ክርስቲያን መጥተው በማየ ገቦ ተጠምቀው ዳግመኛ ከብርሃን ተወልደው ሰይጣንን የሚያስደነግጥ መልክ ይዘው ወደየቤታቸው ይመለሳሉ፡፡ ያስተውሉ! ደብረ ታቦር የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናት፡፡ በደብረ ታቦር ነቢያትና ሐዋርያት፣ መዓስባንና ደናግል፣ አረጋውያንና ወጣቶች እንደ ተገኙ ዅሉ ቤተ ክርስቲያንም በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ የታነጸች፤ ለመዓስባንና ለደናግል፣ ለአረጋውያንና ለወጣቶች ለመላው ሕዝበ ክርስቲያን የተዘጋጀች የእግዚአብሔር መገለጫ ተራራ ናት፡፡ ከነቢያት ሁለቱ፤ ከሐዋርያት ሦስቱ መገኘታቸው ዛሬ በቤተ መቅደስ የሚያገለግሉት አምስት ልዑካን ምሳሌ ነው፡፡ እነዚያ ክርስቶስን እንደ ታቦት በመኻል አድርገው እንደ ተገኙ፣ ዛሬም ልዑካኑ (አገልጋዮች) በቤተ ክርስቲያን በቃል ኪዳኑ ታቦት ዙሪያ የክብሩን ዙፋን ከበው ይቆማሉ፡፡

የፀረ ተሐድሶ አገልግሎት በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት

ማኅበረ ምእመናን ኦርቶዶክሳዊውን አስተምህሮ በሚገባ እንዲያውቁ የሚያበቃ ትምህርትና ሥልጠና መስጠት፤ በየዐውደ ምሕረቱ የሚቀርበው ትምህርተ ወንጌል በስፋት እንዲቀጥል መደገፍ፤ የአፅራረ ቤተ ክርስቲያን እንቅስቃሴ እንዲዳከምና ኦርቶዶክሳዊው አስተምህሮ እንዲስፋፋ ማድረግ፤ ሐሰተኞች መምህራንን በመከታተል ከስሕተታቸው እንዲታረሙ መምከር፤ ካልተመለሱም ተወግዘው እንዲለዩ ለቅዱስ ሲኖዶስ ማቅረብ ኮሚቴው ወደፊት ለማከናወን ያቀዳቸው ተግባራት መኾናቸውን ሊቀ ጉባኤ ቆሞስ አባ ተክለ ሃይማኖት ጨምረው ገልጸዋል፡፡ አያይዘውም አፅራረ ቤተ ክርስቲያን በተለይ ራሳቸውን ‹ተሐድሶ› ብለው የሚጠሩ መናፍቃን ማን ይነካናል ብለው በድፍረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እየተሳደቡ፣ አባቶችንም እያጥላሉ እንደ ኾነ፤ የተሳሳተ ትምህርታቸውን ለማስፋፋት ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ እንደሚገኙ፤ ቍጥራቸውም በዘመናት ሳይኾን በቀናት እየጨመረ እንደ መጣ ጠቅሰው፣ በሀገረ ስብከቱ የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴ የተቋቋመው እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ ይህን የመናፍቃኑን እንቅስቃሴ ለመከላከል መኾኑን አብራርተዋል፡፡