የወደቁትን እናንሣ
ጕብኝት ባደረግንበት ወቅት እንዳስተዋልነው በማኅበሩ እየተጦሩ ከሚገኙ ወገኖች መካከል አንዳንዶቹ የአብነት መምህራን፣ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች፣ በመንግሥትና በግል ድርጅቶች ሓላፊነት የነበራቸው ሰዎች ናቸው፡፡ እነዚህ የቤተ ክርስቲያንና የአገር ባለውለታዎች በሕመም፣ በጤና እና በእርጅና ምክንያት የአልጋ ቁራኛ፣ የደዌ ዳኛ ኾነው ጎዳና ላይ በወደቁበት ወቅት ይህ ማኅበር ደርሶላቸው አስፈላጊውን ዅሉ ድጋፍ እያደረገላቸው ይገኛል፡፡ በተለይ የአእምሮ ሕሙማንና ከአንድ በላይ በኾነ የጤና እክል የተጠቁ ማለትም የማየትም የመስማትም የመንቀሳቀስም ችግር ያለባቸውና ሰውነታቸውን መቈጣጠር የማይችሉ አባቶች፣ እናቶች፣ ወንድሞችና እኅቶች ኹኔታ ልብን ይነካል፡፡ እነዚህ ወገኖች የሚንቀሳቀሱትም፣ የሚመገቡትም፣ የሚለብሱትም፣ የሚጸዳዱትም በሰው ርዳታ ነው፡፡ እነርሱን ያየ ሰው የማኅበሩን ዓላማ በግልጽ ይረዳዋል የሚል እምነት አለን፡፡