‹‹ለሰዎች ትታዩ ዘንድ፥ ምጽዋታችሁን በሰዎች ፊት እንዳታደርጉ ተጠንቀቁ!›› (ማቴ. ፮፥፩)
ክርስቲያኖች የሚመጸውቱት ከተረፋቸው ሳይሆን ካላቸው ነው፤ ለዚህም ምክንያቱ ደግሞ አስቀድመን እንዳየነው ምጽዋት ትልቅ የክርስትና ቁልፍ በመሆኗ ነው፡፡ ብዙዎቻችን የኃጢአት ሥር በተባለው በገንዘብ መውደድ ልባችን ስለታሰረ ምጽዋት የሚመስለን ከተትረፈረፈው ኪሳችን አንድ ብር ለነዳይ መስጠት ነው፡፡ ምጽዋት ብድሩ ከልዑል እግዚአብሔር ይገኛል በሚል እምነት ለተቸገሩ ሰዎች የሚሰጥ ልግስና እንደመሆኑ አቀራረቡ ከግብዝነትና ከከንቱ ውዳሴ የጠራ መሆን እንዳለበት ጌታችን አስተምሯል፡፡ የድሆችን ጩኸት ሰምቶ በችግራቸው በመድረስ ምላሽ የሚሰጥ እሱ በተቸገረ ጊዜ በጎ ምላሽ ከእግዚአብሔር ዘንድ ያገኛል፡፡ ምጽዋት የክፉ ጊዜ ዋስትና ነውና፡፡ (ሉቃ፳፩÷፩-፬)