ክረምት – የመጀመርያ ክፍል

በመጋቤ ሐዲስ ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

ነሐሴ ፳፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹ክረምተ ወሐጋየ ዘአንተ ፈጠርከ፤ በጋንም ክረምትንም አንተ አደረግህ፤›› (መዝ. ፸፫፥፲፯) በማለት ቅዱስ ዳዊት እንደ ገለጸው እግዚአብሔር አምላክ የዓለምን ምግብ ሥጋዊውንም መንፈሳዊውንም በአራት ወቅት ከፍሎታል፡፡ ሥጋዊውን በአራቱ ክፍላተ ዘመን፤ መንፈሳዊውን በአራቱ ወንጌላዊያን ትምህርት፡፡ የሰው ልጅ ሥጋዊ ምግብና ከአራቱ ክፍላተ ዘመን እንደማይወጣ ዅሉ መንፈሳዊ ምግብናውም ከአራቱ ወንጌላውያን አይወጣም፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር የሥጋም የነፍስም ፈጣሪ፣ መጋቢ ነውና፡፡ ከአራቱ ክፍላተ ዘመን አንዱ አሁን የምንገኝበት ዘመነ ክረምት ነው፡፡ በዘመነ ክረምት ከሥጋዊ ምግብ ያለፈ መንፈሳዊ ምግብም እናገኛለን፡፡

ክረምት ምንድን ነው?

ክረምት ማለት ‹ከርመ – ከረመ› ካለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲኾን ‹መክረም፣ የዓመት መፈጸም፣ ማለቅ፣ መጠናቀቅ› ማለት ነው፡፡ ክረምት፣ በፀሐይ የደረቁ ኮረብቶች፣ ተራሮች በዝናም አማካይነት ውኃ የሚያገኙበትና በልምላሜ የሚሸፈኑበት፤ የደረቁ ወንዞች፣ ጉድጓዶች በውኃ የሚሞሉበት፤ በፀሐይ የተቃጠለች ምድር ከሰማይ በሚወርድ ጠል በረከት የምትረካበት፤ በውኃ ጥም የተሰነጣጠቁ የምድር ጉረሮዎች ውኃን የሚጠግቡበት፤ ሰማይ በደመና፣ የተራሮች ራስ በጉም የሚሸፈኑበት፤ በሙቀት ፋንታ ቅዝቃዜ፣ በድርቅ ፈንታ ልምላሜ የሚነግሥበት፤ ተሰባብሮ የወደቀ ሐረግ (ተክል) ቀና ብሎ የሚቆምበት፣ የሚያድግበት ወቅት ነው፡፡

፩. ክረምት ወርኃ ማይ (የውኃ ወቅት) ነው

ውኃ፣ እግዚአብሔር አምላክ ለፈጠረው ፍጥረት ዅሉ በጣም አስፈላጊ ፍጥረት ነው፡፡ ምድር የዘሩባትን እንድታበቅል፣ የተከሉባትን እንድታጸድቅ፣ ያጸደቀችውን ተክልም ለፍሬ እንድታበቃ ውኃ አስፈላጊ ነው፡፡ ያለ ውኃ ለምግብነት የሚውል ነገር በዓለማችን ውስጥ የለም፡፡ ምግብ የሚዘጋጀውም የሚወራረደውም በውኃ ነው፡፡ ‹‹ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡ? ውኃ ቢያንቅ በምን ይውጡ?›› በማለት አበው የውኃን ጥቅም ያስረዳሉ፡፡ ቁሳቁሱ የሚታጠበው፤ ቤት የሚሠራው፤ ሕንጻ የሚገነባው በውኃ ነው፡፡ በባሕርም በየብስም ለሚኖሩ፤ ለምግብነት ለሚዉሉትም ለማይዉሉትም ውኃ አስፈላጊ ነው፡፡ እንስሳትም፣ እፀዋትም፣ ምድርም ውኃ ይፈልጋሉ፡፡ በጠቅላላው የፍጡራን ሕይወት የውኃ ጥገኛ ነው፡፡ የሰው ልጅ የሚጠቀምባቸው ፍጡራን ዅሉ ያለ ውኃ ምግብ አይሰጡም፡፡ ስለዚህ ከፍጡራን በተለየ መልኩ ውኃ ለሰው ልጅ ያስፈልገዋል፡፡ በዓለማችን ብዙውን ቦታ የሚሸፍነው ውኃ መኾኑን ሥነ ፍጥረትም ሳይንስም ይስማሙበታል፡፡ ምክንያቱም በምድር ላይ ካለ ፍጡር ውኃ የማያስፈልገው የለምና፡፡

ከዚህ አለፍ ብለን ስንመለከት በአርአያ ሥላሴ የተፈጠረ የሰው ልጅ ከተፈጠረባቸው አራት ባሕርያት አንዱ ውኃ ነው፡፡ የሰው ልጅ በመሬትነት ባሕርዩ እየፈረሰና እየተቆረሰ ዓለምን እንዳያጠፋ በውኃነት ባሕርዩ አንድነቱ ጸንቶለት ይኖራል፡፡ በእሳትነት ባሕርዩ ዓለምን እንዳያቃጥል በውኃነት ባሕርዩ እየቀዘቀዘ ይኖራል፡፡ ሰው ከእናቱ ተወልዶ የእናቱን ጡት ጠብቶ እንዲያድግ ሰውም ከውኃ፣ ከእሳት፣ ከነፋስና ከመሬት ተፈጥሮ እነዚሁ የተገኘባቸውን እየተመገበ በምድር ይኖራል፡፡ የአራቱ ባሕርያት አስታራቂ ሽማግሌ ውኃ ነው፡፡ ጠበኞች የኾኑ ነፋስና መሬት በውኃ ይታረቃሉ፡፡ ነፋስ መሬትን ይጠርገዋል፡፡ መሬትም ነፋስን ይገድበዋል፡፡ ዝናም በዘነመ ጊዜ ትቢያው (የመሬት ላይኛው ክፍል) በውኃ አማካይነት ከታችኛው ክፍል ጋር አንድ ይኾናል፤ በነፋስ ከመወሰድም ይተርፋል፡፡

ከዚህም ሌላ ውኃ የእግዚአብሔር መሣሪያ ነው፡፡ የሰው ልጆች ሕገ እግዚአብሔርን ሲጥሱ፣ ትእዛዘ እግዚአብሔርን ሲያፈርሱ ከሥርዓቱ ሲወጡ፣ ከአምልኮቱ ሲያፈነግጡ ውኃ መቅጫ መሣሪያ ነው፡፡ ለምሳሌ በኀጢአት የተበላሸው፣ የቆሸሸው ዓለም የተቀጣው በውኃ ነው (ዘፍ. ፮፥፩፤ ፯፥፩፤ ፰፥፩)፡፡ ነቢዩ ኤልያስ፣ አምልኮተ እግዚአብሔርን በአምልኮተ ጣዖት ተክተው፣ ሃይማኖተ ኦሪትን ትተው፣ የጣዖት ውሽማ አበጅተው ያስቸገሩትን አክአብና ኤልዛቤልን እንደዚሁም መሰሎቻቸውን የቀጣው ዝናም ለዘር፣ ጠል ለመከር እንዳይሰጥ ሰማይን ለጉሞ፣ ዝናምን አቁሞ ነው፡፡ በአንጻሩ በረድና እሳት አዝንሞ እንደ ነበርም መጽሐፍ ቅዱስ ያስረዳናል፡፡ ‹‹ኤልያስ እንደኛ የኾነ ሰው ነበር፡፡ ዝናም እንዳይዘንም አጥብቆ ጸለየ፤ በምድርም ላይ ሦስት ዓመት ከስድስት ወር ዝናም አልዘነበም፡፡ ሁለተኛም ጸለየ፤ ሰማዩም ዝናብን ሰጠ፤ ምድር ፍሬዋን አበቀለች፤›› በማለት ሐዋርያው እንደ ተናገረው (ያዕ. ፭፥፲፯)፡፡

ውኃ እስከ አሁን የተመለከትነው በሥጋዊ ምግብነቱ የሚሰጠውን አገልግሎት ነው፡፡ ውኃ መንፈሳዊ ምግብና (ምግብነት ወይም አገልግሎት) አለው፡፡ ደገኛዋ የሰው ልጆች ጥምቀት በውኃ መፈጸሟ የውኃ ጥቅም የጎላ መኾኑን ያሳየናል፡፡ የጥምቀታችን መሥራች ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአባቶቻችንና በእኛ ላይ የነበረውን የዕዳ ደብዳቤ ያጠፋልን በውኃ ተጠምቆ ነውና (ማቴ. ፫፥፲፫)፡፡ ‹‹ከውኃና ከመንፈስ ያልተወለደ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ዮሐ. ፫፥፭)፡፡ ይኸውም ውኃ ከሥጋዊ ምግብናው ባሻገር እኛ የእግዚአብሔር ልጆች የምንኾንበት ምሥጢር መፈጸሚያ መኾኑን ያስረዳል፡፡ በሌላ መልኩ ጌታችን የእኛን ሥጋ ለብሶ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተገልጾ ባስተማረ ጊዜ ‹‹እንጀራ ለመነ›› ሳይኾን ‹‹ውኃ ለመነ›› ተብሎ ነው የተነገረለት፡፡ ‹‹ውኃ አጠጪኝ አላት›› እንዲል (ዮሐ. ፬፥፯)፡፡ እስራኤልን ዐርባ ዓመት ውኃ ከጭንጫ እያፈለቀ ያጠጣ አምላክ ውኃ የለመነው ውኃ አጥቶ አይደለም፡፡ ውኃ ትልቅ ምሥጢር የሚፈጸምበት መኾኑን ለመግለጽ ነው እንጂ፡፡ ይኸውም ሊታወቅ ‹‹የእግዚአብሔርን ስጦታና ውኃ አጠጪኝ የሚልሽ ማን መኾኑን ብታውቂስ አንቺ ደግሞ በለመንሺው፤ እርሱም የሕይወትን ውኃ በሰጠሸ ነበር … እኔ ከምሰጠው ውኃ የሚጠጣ ለዘለዓለም አይጠማም፤›› በማለት አስተምሮአል፡፡

ጌታችን በመስቀል ላይ ከተናገራቸው ሰባቱ ንግግሮች አንዱ ‹‹ተጠማሁ›› የሚል ነበር (ዮሐ. ፲፱፥፳፱)፡፡ ይህ ከሥጋ መጠማት ያለፈ የእኛን የነፍሳችን ጥማት እንደ አጠፋልን የምንማርበት ነው፡፡ እኛን የሕይወት ውኃ ያጠጣን ዘንድ ተጠማሁ አለም፤ በዓለም ላሉ ፍጡራን ዅሉ ውኃ አስፈላጊ ቢኾንም ቅሉ በተለይ ለሰው ልጆች እጅግ አስፈላጊ እንደ ኾነ ሲያስረዳም ነቢዩ ኢሳይያስ እንዲህ ሲል ተናገረ፤ ‹‹እናንተ የተጠማችሁ ዅሉ ወደ ውኃ ኑ፤ ገንዘብም የሌላችሁ ኑና ግዙ፤›› (ኢሳ. ፶፭፥፩)፡፡ ‹‹የተጠማ ይምጣ፤ ይጠጣ፤›› የሚለው ኃይለ ቃል ብዙ ምሥጢር አለው፡፡ ጌታችን የአይሁድ በዓል በሚከበርበት ቦታ ተገኝቶ ቀደም ሲል በኢሳይያስ የተነገረው ቃል ስለ መንፈስ ቅዱስ የተነገረ መኾኑን ገልጿል፡፡ ‹‹ኢየሱስም ቆሞ ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ፡፡ በእኔ የሚያምን መጽሐፍ እንዳለ የሕይወት ውኃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል ብሎ ጮኸ፡፡ ይኼን ግን በእርሱ የሚያምኑ ሊቀበሉት ስለ አላቸው ስለ መንፈስ ቅዱስ ተናገረ፤›› እንዲል (ዮሐ. ፯፥፴፯-፴፱)፡፡ ስለዚህ ውኃ የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌ ኾኗል ውኃ ከቆሻሻ፣ ከዕድፍ እንዲያነጻ መንፈስ ቅዱስም ከኀጢአት፣ ከርኵሰት፣ ከክፋት፣ ከተንኮል፣ ከበደል ሰውን ያነጻልና፡፡

፪. ክረምት ወርኃ ዘር (የዘር ወቅት) ነው

ገበሬው በበጋ ያረሰውን የከሰከሰውን ደረቅ መሬት በዝናብ ወቅት አለስልሶ አዘጋጅቶ ከጎታው ወይም ከጎተራው ያስቀመጠውን ዘር ባዘጋጀው መሬት ላይ አውጥቶ ይዘራል፡፡ መሬቱ ያብቅል አያብቅል ፍሬ ይስጥ አይስጥ ሳያውቅ እግዚአብሔር በዝናብ አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ ይመግበኛል ብሎ በማመን ያለ ምንም ጥርጥር የጎታውን እኽል ለመሬት አደራ ይሰጣል፡፡ ከላይ ዝናሙን ከታች ጭቃውን ታግሦ በሬዎችን እየነዳ በትከሻው ላይ ዘርና ቀምበር ተሸክሞ ዘር ለመዝራት ይሰማራል፡፡ የገበሬውን ኹኔታ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲህ ብሎ ገልጾታል፤ ‹‹ዘሪ ሊዘራ ወጣ፤ ሲዘራም አንዳንዱ ዘር ከመንገድ ዳር ወደቀ፡፡ በጭንጫ ላይ የወደቀ ዘር አለ፡፡ በእሾኽ መካከል የወደቀ ዘርም አለ፡፡ በመልካም መሬት ላይም የወደቀ ዘር አለ፡፡ መቶ፣ ስልሳ፣ ሠላሳ ፍሬ ሰጠ፤›› (ማቴ. ፲፫፥፩)፡፡ ጌታችን ራሱን በገበሬ፣ ቃሉን በዘር፣ የሰማዕያንን ልቡና በመንገድ፣ በዐለት፣ በእሾኽ፣ በለሰለሰ መሬት መስሎ አስተምሯል፡፡ በመንገድ የተመሰለው ሰምተው የማያስተውሉ ሰዎች ልቡና ነው፡፡ የሰማይ ወፎች የተባሉ ደግሞ አጋንንት ናቸው፡፡ ‹‹ኢትሕሚ ሰብአ በቤትከ እስመ ዖፈ ሰማይ ያወጽዖ ለነገርከ፤ የሰማይ ወፍ (ሰይጣን) ቃልህን ያወጣዋልና፣ ክንፍ ያለውም ነገርህን ያወራዋልና በልብህ ዐሳብ እንኳን ቢኾን ንጉሥን አትሳደብ፤ በመኝታ ቤትህም ባለ ጠጋን አትማ፤›› እንዳለ ጠቢቡ ሰሎሞን (መክ. ፲፥፳)፡፡

በዐለት የተመሰሉት ፈጥነው የሚሰሙ ግን ተግባር ላይ የሌሉ በእሾኽ የተመሰሉትም የዚህ ዓለም ዐሳብ፣ ምድራዊ ብልጽግና፣ ፍቅረ ዓለም አስሮ የያዛቸው ሰዎች ናቸው፡፡ በመልካም መሬት የተመሰሉት ደግሞ ቃሉን ሰምተው የጽድቅ ሥራን የሚሠሩ ናቸው፡፡ በወርኃ ዘር የምንማረው ትልቁ ትምህርት ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን ነው፡፡ በወርኃ ማይ ምሥጢረ ጥምቀትን እንደተማርን ገበሬው በጎታው ያከማቸውን እኽል ከአፈር ጋር አንድ እንደሚያደርገው ማለት በአፈር ላይ እንደሚዘራው የሰው ዘርም እንዲሁ ‹‹ውሎ ውሎ ከቤት ኖሮ ኖሮ ከመሬት›› እንዲሉ ሲሞት በመቃብር ከአፈር ጋር አንድ ይኾናል፤ ይፈርሳል ይበሰብሳል፤ ወደ አፈርነቱ ይመለሳል፡፡ ‹‹ወደ ወጣህበት መሬት እስክትመለስ ድረስ በፊትህ ወዝ እንጀራን ትበላለህ፡፡ አፈር ነህና ወደ አፈርነትህም ትመለሳለህና፤›› እንዳለ (ዘፍ. ፫፥፲፱)፡፡

ይቆየን

በአሜሪካ ለአራተኛ ጊዜ ዐውደ ርእይ ተካሔደ

በአሜሪካ ማእከል

ነሐሴ ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ›› በሚል ርእስ ማኅበረ ቅዱሳን ያዘጋጀው ፭ኛው ዙር ልዩ ዐውደ ርእይ በአሜሪካ አገር ለአራተኛ ጊዜ ለተመልካቾች ቀረበ፡፡

ዐውደ ርእዩ በአሜሪካ ማእከል በካሮላይና ግንኙነት ጣቢያ አስተባባሪነት ነሐሴ ፲፫ እና ፲፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በሻርሎት ከተማ በሚገኘው የግሪክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አዳራሽ ቀርቦ በበርካታ ምእመናን ተጐብኝቷል፡፡

በመክፈቻ ሥርዓቱ ላይ የየአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ሰባክያነ ወንጌል፣ ቀሳውስት፣ ዲያቆናትና በርካታ ምእመናን የተገኙ ሲኾን፣ በአባቶች ጸሎት ከተከተፈተ እና በግንኙነት ጣቢያው የእንኳን ደኅና መጣችሁ መልእክት ከተላለፈ በኋላ ዐውደ ርእዩ በሁለቱም ቀናት ለተመልካቾች ክፍት ኾኖ ቆይቷል፡፡

ከአባቶች ካህናትና ከአዋቂ ምእመናን በተጨማሪ በእንግሊዝኛ ቋንቋ የሚግባቡ በርካታ ታዳጊ ሕፃናትና ወጣቶችም በዐውደ ርእዩ መሳተፋቸውን ግንኙነት ጣቢያው በሪፖርቱ አስረድቷል፡፡

እንደ ግንኙነት ጣቢያው ማብራሪያ የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ይመለከተኛል የሚሉ ምእመናን እየተበራከቱ መምጣታቸውን የዐውደ ርእዩ ተመልካቾቹ ያቀርቧቸው ከነበሩ አስተያየቶች ለመረዳት ተችሏል፡፡ ይህም የዐውደ ርእዩ ዓላማ መሳካቱን እንደሚያመላክት በሪፖርቱ ተጠቅሷል፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም የአንድ ለአንድ ድጋፍ በማድረግ የአብነት ተማሪዎችን ለመርዳትና ለማስተማር ቃል የገቡ ምእመናን እንደ ነበሩም ግንኙነት ጣቢያው ጨምሮ ገልጿል፡፡

በመርሐ ግብሩ ማጠቃለያ ዕለት ቃለ መጠይቅ የተደረገላቸው አንዳንድ ምእመናን በዐውደ ርእዩ በመሳተፋቸው ደስተኞች መኾናቸውን ገልጠው ማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎቱን በአገር ውስጥ ብቻ ሳይገድብ ከኢትዮጵያ ውጪ ለሚኖሩ ምእመናንም ትምህርተ ወንጌል እንዲዳረስ የሚያደርገውን ጥረት አድንቀዋል፡፡ ይህ የማኅበሩ አገልግሎት ተጠናክሮ ሊቀጥል፣ ዐውደ ርእዩም በመላው ዓለም ሊዳረስ እንደሚገባው አስተያየት ሰጪዎቹ አሳስበዋል፡፡

በመጨረሻም ዐውደ ርእዩ በስኬት መጠናቀቁን ያስታወቀው የካሮላይና ግንኙነት ጣቢያ ጽ/ቤት እና የዝግጅት ኮሚቴው በልዩ ልዩ መንገድ አስተዋጽዖ ላደረጉ የቤተ ክርስቲያን አባቶች፤ ለአታላንታ ንዑስ ማእከልና ሰንበት ትምህርት ቤት አባላት፤ በተለይ ከአራት ሰዓታት በላይ ተጕዘው በትዕይንት ገላጭነት ለተሳተፉ ወንድሞች እና እኅቶች፤ እንደዚሁም ለበጎ አድራጊ ምእመናን በማኅበረ ቅዱሳን ስም ምስጋና አቅርቧል፡፡

የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ዕረፍት

በዝግጅት ክፍሉ

ነሐሴ ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ቅዱሳን ጻድቃን በሕይወተ ሥጋ እያሉ፣ ከሞቱም በኋላ (በዐጸደ ነፍስ ኾነው) በጸሎታቸው ለሚታመኑ፤ በቃል ኪዳናቸው ለሚማጸኑ ምእመናን የድኅነተ ሥጋ፣ የድኅነት ነፍስ ምክንያቶች ናቸው፡፡ ቅዱሳን ጻድቃን በመንፈሳዊ አርአያነታቸው፣ በጸሎታቸውና በትምህርታቸው ከከበቡን የነፍስ ጠላቶች፤ ከርኲሳን መናፍስትና ከጨለማው ልጆች፤ ከክፉ ሰዎች ሽንገላና ተንኰል ለመጠበቅ ከእግዚአብሔር የተቀበሉት ሥልጣን ምን ጊዜም ይሠራል፡፡ በጻድቃን መኖር አገር ከጥፋት ትድናለች፡፡ የጻድቃንን ስም ጠርቶ እግዚአብሔርን በመለመን በረከትና ረድኤት ይገኛል፡፡ ስለ ጻድቃን ብሎ እግዚአብሔር ምሕረቱን ያድላል፡፡ ጻድቃንን ማሰብ፣ ሥራቸውንም መዘከር ክርስቲያናዊ ሕይወታችንን ያጐለምስልናል፡፡ በነፍስ በሥጋም ይጠብቀናል፤ ይረባናል፤ ይጠቅመናል፡፡ ስለዚህም ነው ቤተ ክርስቲያናችን ጻድቃንን እንድናስባቸው፤ በስማቸውም ለድሆችና ለጦም አዳሮች እንድንመጸውት፤ መታሰቢያቸውንም እንድናደርግ የምትመክረን፣ የምታስተምረን፡፡ ከእነዚህ ቅዱሳን መካከል መካከል ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንዱ ናቸው፡፡

አቡነ ተክለ ሃይማኖት በእግዚአብሔር መልካም ፈቃድ፤ በሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ብሥራት ከአባታቸው ከካህኑ ጸጋ ዘአብ እና ከእናታቸው ከቅድስት እግዚእ ኃረያ ታኅሣሥ ፳፬ ቀን ፲፪፻፲፪ (1212) ዓ.ም በቡልጋ አውራጃ ኢቲሳ በሚባል ቦታ ተወለዱ፡፡ (ቦታው በአሁኑ ሰዓት ደብረ ጽላልሽ ኢቲሳ ተክለ ሃይማኖት ተብሎ ይጠራል)፡፡ በተወለዱ በሦስተኛው ቀን እሑድ ከጠዋቱ በሦስት ሰዓት ከእናታቸው ዕቅፍ ወርደው ‹‹አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ፤ አንዱ አብ ቅዱስ ነው፤ አንዱ ወልድ ቅዱስ ነው፤ አንዱ መንፈስ ቅዱስ ቅዱስ ነው›› በማለት ሥላሴን አመስግነዋል፡፡ በተወለዱ በ፲፭ ዓመታቸው መዓርገ ዲቊናን፤ በ፳፪ ዓመታቸው ደግሞ መዓርገ ቅስናን ከግብጻዊው ጳጳስ አባ ጌርሎስ (ቄርሎስ) ተቀብለዋል፡፡

ወላጆቻቸው ያወጡላቸው ስም ‹ፍሥሐ ጽዮን ነው፡፡ በአንድ ወቅት ሕፃኑ ፍሥሐ ጽዮን ወደ ጫካ ለአደን ሔዱ፡፡ በዚያች ዕለት ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጦ ጸጋ መንፈስ ቅዱን አሳደረባቸው፡፡ ለሐዋርያዊ አገልግሎት ወንጌል ወዳልተዳረሰበት ቦታ እንደሚልካቸውም አስረዳቸው፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም ከአውሬ አዳኝነት ሰውን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመመለስ እንደ ተመረጡ፤ አጋንንትን የማውጣት፣ ተአምራትን የማድረግ ሥልጣን እንደ ተሰጣቸው፤ ስማቸውም ተክለ ሃይማኖት እንደሚባል፤ ትርጓሜውም ተክለ አብ፣ ተክለ ወልድ፣ ተክለ መንፈስ ቅዱስ ማለት እንደ ኾነ አበሠራቸው፡፡ ከዚህ በኋላ ያላቸውን ንብረት ዅሉ ለቤተ ክርስቲያንና ለነዳያን ሰጥተው ‹‹አቤቱ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! የመንግሥተ ሰማያትን በር ትከፍትልኝ ዘንድ እነሆ ቤቴን እንደ ተከፈተ ተውኹልህ›› በማለት ቤታቸውን ትተው ወንጌልን ለማስተማር ፈጥነው ወጡ፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምረው በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ ወንጌልን በመስበክና ተአምራትን በማድረግ ብዙ አሕዛብን ከአምልኮተ ጣዖት ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር፤ ከገቢረ ኀጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ መልሰዋል፡፡ አብያተ ክርስቲያናትንም አሳንጸዋል፡፡

ከዚህ በኋላ በደብረ ሊባኖስ ገዳም (ገዳመ አስቦ) ዋሻ በመግባትም ሁለቱን በፊት፣ ሁለቱን በኋላ ሁለቱን በቀኝ፣ ሁለቱን በግራ ስምንት ጦሮችን ተክለው እጆቻቸውን በትእምርተ መስቀል በመዘርጋት የክርስቶስን ሕማም፣ ሞትና ነገረ መስቀል በማሰብ በተመስጦ ሌሊትና ቀን ያለ ማቋረጥ በጾም፣ በጸሎት ተወስነው ሲጋደሉ፤ ከቊመት ብዛት የተነሣ በ፺፪ኛ ዓመታቸው ጥር ፬ ቀን ፲፪፻፹፱ (1289) ዓ.ም አንዲቱ የእግራቸው አገዳ ተሰብራለች፡፡ ደቀ መዛሙርቱም የመንፈሳዊ አባታቸውን ስባረ ዐፅም (የዐፅም ስባሪ) አክብረው በሥርዓት አኑረዋታል፡፡ እግራቸው እስኪሰበር የቆዩባቸው ዓመታትም ፳፪ ናቸው፡፡ ለሰባት ዓመታት በአንድ እግራቸው ቆመው ያለ ምግብና ያለ ውኃ በትኅርምት ሌሊትና ቀን እንደ ምሰሶ ጸንተው በትጋት ለሰው ዘር ዅሉ ድኅነትን ሲለምኑ ኖረዋል፡፡ ከሰባቱ ዓመታት ውስጥ ጥቂት ውኃ የቀመሱት በአራተኛው ዓመት ብቻ እንደ ነበረ መጽሐፈ ገድላቸው ይናገራል፡፡

ጻድቁ አባታችን ምድራዊ ሕይወታቸውን በተጋድሎና በሐዋርያዊ አገልግሎት ከፈጸሙ በኋላ ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ የሚያልፉበት ቀን ተቃረበ፡፡ በዚህ ጊዜ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም፣ ከቅዱሳን መላእክት፣ ከቅዱሳን ነቢያትና ከቅዱሳን ሐዋርያት ጋር ወደ እርሳቸው በመምጣት የሚያርፉበት ዕለት መድረሱን ነገራቸው፡፡ የተጋድሏቸውን ጽናት አድንቆ በስማቸው መታሰቢያ ለሚያደርጉ፣ ለነዳያን ለሚመጸዉቱ ቤተ ክርስቲያን ለሚያሠሩ የምሕረት ቃል ኪዳን ሰጥቷቸው በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ ስለ ተጋድሏቸው ጽናትም ‹‹በሰው እጅ የማይለካውን ይህንን የመንግሥት አዳራሽ ውሰድ›› በማለት የመለኮትን ነገር የሚናገር የእሳት አንደበት ያለው የጸጋ ልብስ አልብሷቸዋል፤ በመስቀል ምልክት ያጌጡ ሰባት የሕይወት አክሊላትንም አቀዳጅቷቸዋል፡፡

አቡነ ተክለ ሃይማኖት የዕረፍታቸው ጊዜ መቃረቡን ባወቁ ጊዜ የመንፈስ ልጆቻቸውን ጠርተው ጌታችን የነገራቸውን ዅሉ አስረድተው አባታዊ ምክርና ተግሣፅ ከሰጧቸው በኋላ ነሐሴ ፳፬ ቀን ከዚህ ዓለም ድካም ዐርፈዋል፡፡ የመንፈስ ልጆቻቸውም ለአንድ ቅዱስ አባትና ካህን በሚገባ ሥርዓት በማኅሌት፣ በዝማሬና በምስጋና ቀብረዋቸዋል፡፡ ጌታችንም ከእመቤታችንና ከቅዱሳን መላእክት ጋር ተገልጾላቸዋል፤ ነፍሳቸውንም ‹‹የጠራሽ፣ ንጽሕት ነፍስ ሆይ ወደ እኔ ነዪ›› ብሎ በክብር ተቀብሏታል፡፡ በመጽሐፈ ገድላቸው እንደ ተጠቀሰው አቡነ ተክለ ሃይማኖት በዚህ ዓለም የኖሩበት ዕድሜ ዘጠና ዘጠኝ ዓመት ከዐሥር ወር ከዐሥር ቀን ነው፡፡ በእናት አባታቸው ቤት ፳፪ ዓመት፤ በከተታ ፫ ዓመት፤ በይፋት ፱ ወር፤ በዳሞት ፲፪ ዓመት፤ በአማራ ፲ ዓመት፤ በሐይቅ ፲ ዓመት፤ በደብረ ዳሞ ፲፪ ዓመት፤ በትግራይና በኢየሩሳሌም ገዳማት ፩ ዓመት፤ ዳዳ በሚባል አገር ፩ ወር፤ በደብረ አስቦ ገዳም ፳፱ ዓመት ከ፲ ቀን መቆየታቸውን መጽሐፈ ገድላቸው ይናገራል (ገ.ተ.ሃ ፶፱፥፲፬-፲፭)፡፡

በአጠቃላይ ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሕይወታቸዉን ሙሉ ለእግዚአብሔር በመስጠት፣ እንደ በሬ ተጠምደው፣ እንደ ገበሬ ታጥቀው ይህንን ዓለም ንቀው፣ በጾም በጸሎት ተወስነው በብሕትውና ከመኖራቸው ባሻገር እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ወንጌልን በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ የሰበኩ፤ በጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ድውያነ ሥጋን በተአምራት፣ ድውያነ ነፍስን በትምህርት የፈወሱ ሐዋርያ ናቸው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያችንም ‹‹እናንተን የሚቀበል እኔን ይቀበላል፤ እኔንም የሚቀበል የላከኝን ይቀበላል፡፡ ነቢይን በነቢይ ስም የሚቀበል የነቢይን ዋጋ ያገኛል፡፡ ጻድቅንም በጻድቅ ስም የሚቀበል የጻድቁን ዋጋ ያገኛል፡፡ ማንም ከእነዚህ ከታናናሾቹ ለአንዱ ቀዝቃዛ ጽዋ ብቻ በደቀ መዝሙር ስም የሚያጠጣ እውነት እላችኋለሁ፤ ዋጋው አይጠፋበትም›› (ማቴ. ፲፥፵-፵፪) በማለት ጌታችን የተናገረውን መለኮታዊ ቃል ኪዳን መሠረት አድርጋ መጋቢት ፳፬ ቀን የፅንሰታቸውን፤ ታኅሣሥ ፳፬ ቀን የልደታቸውን፤ ጥር ፬ ቀን የስባረ ዐፅማቸውን (እግራቸው የተሰበረበትን)፤ ግንቦት ፲፪ ቀን የፍልሰተ ዐፅማቸውን፤ ነሐሴ ፳፬ ቀን የዕረፍታቸውን በዓል በትላቅ ደስታ ታከብራለች፡፡ የጻድቁ በረከት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡-

  • መለከት መጽሔት ፲፰ኛ ዓመት፣ ቍጥር ፱፡፡
  • መጽሐፈ ስንክሳር፣ ነሐሴ ፳፬ ቀን፡፡
  • ገድለ ተክለ ሃይማኖት፡፡

ዘመነ ክረምት – ክፍል ስድስት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ተከታታዮች! በክፍል አምስት ዝግጅታችን ሦስተኛውን የዘመነ ክረምት ንዑስ ክፍል በተለይ ደሰያትን እና ዓይነ ኵሉን መነሻ በማድረግ ወቅቱን የሚመለከት ትምህርት አቅርበን ነበር፡፡ በዚህ ዝግጅት ደግሞ አራተኛውን የዘመነ ክረምት ንዑስ ክፍል የሚመለከት ትምህርት ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡ መልካም ንባብ!

፬. ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን፣ መዓልት

ከነሐሴ ፳፰ እስከ ጳጕሜን ፭ (፮) ቀን (ከአብርሃም እስከ ዮሐንስ ዋይዜማ) ድረስ ያለው አራተኛው ክፍለ ክረምት ‹ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን መዓልት› ይባላል፡፡ በዚህ ክፍለ ክረምት ውስጥ በሚገኙ ቀናት እነዚህን ፍጥረታት የሚመለከቱ የቅዱሳት መጻሕፍት ክፍሎች በቤተ ክርስቲያናችን ይነገራሉ፤ ይተረጐማሉ፤ ይመሠጠራሉ፡፡ ‹ጎሕ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን፣ መዓልት› ዅሉም የግእዝ ቃላት ሲኾኑ ተመሳሳይ ትርጕምና ጠባይዕ ያላቸው ፍጥረታት ናቸው፡፡ ‹ጎህ፣ ነግህ እና ጽባሕ› – ንጋትን፣ ማለዳን፣ ሌሊቱ ወደ ቀን፤ ጨለማው ወደ ብርሃን የሚሸጋገርበትን ክፍለ ጊዜ ይገልጻሉ፡፡ ብርሃን ደግሞ የጨለማ ተቃራኒ፣ የፀሐይ ብርሃን የማይታይበት ክፍለ ዕለት ሲኾን ‹መዓልት› ማለትም በአንድ በኩል የፀሐይ ብርሃን የሚታይበት ጊዜን፣ በሌላ በኩል ደግሞ ከእሑድ እስከ ሰኞ ያሉትን፣ እንደዚሁም ከ፩ – ፴ የሚገኙ ዕለታትን ያመላክታል (ዘፍ. ፩፥፭-፴፩)፡፡

ስለ ንጋትና ብርሃን ለመናገር በመጀመሪያ ስለ ፀሐይ፣ ስለ ጨረቃ እና ከዋክብት አፈጣጠር በጥቂቱ ማስታወስ ያስፈልጋል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ በዕለተ ረቡዕ በመጀመሪያው ሰዓተ ሌሊት ‹‹ለይኩን ብርሃን፤ ብርሃን ይኹን›› ባለ ጊዜ ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብት ተፈጥረዋል፡፡ ‹‹እግዚአብሔርም ‹ብርሃን ይኹን› አለ፤ ብርሃንም ኾነ፡፡ እግዚአብሔርም ብርሃኑ መልካም እንደ ኾነ አየ፤ እግዚአብሔርም በብርሃኑና በጨለማው መካከል ለየ፤ እግዚአብሔርም ብርሃኑን ‹ቀን›፣ ጨለማውንም ‹ሌሊት› ብሎ ጠራው፤›› እንዲል (ዘፍ. ፩፥፫-፬)፡፡ የፀሐይ ተፈጥሮዋ ከእሳትና ከነፋስ ሲኾን ጨረቃንና ከዋክብትን ደግሞ ከነፋስና ከውኃ አርግቶ ፈጥሯቸዋል፡፡ ሲፈጥራቸውም ከዅሉም ፀሐይን፤ ከከዋክብት ደግሞ ጨረቃን አስበልጦ ነው፡፡ የፈጠራቸውም እርሱ ሊጠቀምባቸው ሳይኾን ለሰው ልጅ እና በዚህ ዓለም ለሚገኙ ፍጥረታት እንዲያበሩ ነው፡፡ እነዚህ የብርሃን ምንጮች (ፀሐይ እና ጨረቃ) ልዩ ልዩ ምሳሌያት አሏቸው፤ ከእነዚህ መካከልም በጻድቃንና በኃጥኣን መመሰላቸው አንደኛው ነው፡፡

ጻድቃን ዅልጊዜ በምግባር፣ በሃይማኖት ምሉዓን በመኾናቸው በፀሐይ፤ ኃጥኣን ደግሞ በምግባር አንድ ጊዜ ሙሉ፣ ሌላ ጊዜ ጐደሎ ማለትም አንድ ጊዜ ደግ ሌላ ጊዜ ክፉ እየኾኑ ግብራቸውን በመለዋወጥ ይኖራሉና በጨረቃ ይመሰላሉ፡፡ የፀሐይ እና ጨረቃ አካሔዳቸው በሰማይና በምድር መካከል ነው፡፡ ጻድቃንም በተፈጥሯቸው ምድራውያን ኾነው ሳሉ ሰማያዊውን መንግሥት ይወርሳሉ፡፡ ፀሐይ እና ጨረቃ ሠሌዳቸው ከነፋስ፣ ከእሳትና ከውኃ ነው፡፡ እነዚህ ሦስቱ ጠባይዓት እርስበርስ ተስማምተው ብርሃንን እንዲሰጡ አድርገዋቸዋል፡፡ ስለዚህም በነፋሱ ፍጥነት፣ በእሳቱ ሙቀት፣ በውኃው ቅዝቃዜ ይስማማቸዋል፡፡ ይህም የመምህራን መንፈሳዊ ቍጣ ምሳሌ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን መምህራን ጠባያቸው እንደ ውኃ የቀዘቀዘ ቢኾንም የእግዚአብሔርን ክብር የሚያቃልሉ፣ ቅዱሳንን የሚጥላሉ፣ የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ የሚፃረሩ መናፍቃን ሲመጡ ግን እንደ ነፋስ በሚፈጥን፣ እንደ እሳት በሚያቃጥል መንፈሳዊ ቍጣ ተነሣሥተው ይገሥፃሉ፤ ይመክራሉ፤ ያስተምራሉ፡፡ አንድም እነዚህ ሦስቱ የፀሐይ እና የጨረቃ ሠሌዳዎች የሥላሴ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ይኸውም እሳት በመለኮት፤ ውኃ በትስብእት፤ ነፋስ በመንፈስ ቅዱስ ይመሰላል (መጽሐፈ ሥነ ፍጥረት፣ አንድምታ ትርጓሜ)፡፡

በሌላ ምሥጢር ስንመለከታቸው ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን፣ መዓልት ወይም ዅሉንም በአጠቃላይ በብርሃን ምንጭነት ወይም በብርሃን ብንሰይማቸው የብርሃን ምንጭ ወይም ብርሃን እግዚአብሔር ነው፡፡ እርሱ በጨለማው ዓለም፤ በጨለማው ሕይወታችን፤ በጨለማው ኑሯችን የሕይወትን ወጋገን፣ ንጋት፣ ብሩህ ቀን የሚያወጣ አምላክ ነውና (ዮሐ. ፩፥፭-፲)፡፡ ለዚህም ነው ‹‹እግዚአብሔር ብርሃኔና መድኀኒቴ ነው፤ የሚያስፈራኝ ማነው?›› በማለት ቅዱስ ዳዊት የሚዘምረው (መዝ. ፳፮፥፩)፡፡ ስለ ኾነም እኛ ክርስቲያኖች ብርሃን በተባለ በእግዚአብሔር መታመን ያስፈልገናል፡፡

ዳግመኛም የእግዚአብሔር ሕግ ብርሃን ይባላል፡፡ ብርሃን ጨለማን እንደሚያስወግድ ዅሉ የእግዚአብሔር ሕግም ከኀጢአት ባርነት፣ ከሲኦል እሳት ያድናልና፡፡ ‹‹ሕግህ ለእግሬ መብራት፤ ለመንገዴም ብርሃን ነው›› እንዳለ ቅዱስ ዳዊት (መዝ. ፻፲፰፥፻፭)፡፡ እንደዚሁም ብርሃን ክርስቲያናዊ ምግባርን ያመለክታል፡፡ ብርሃን ለራሱ በርቶ ለሌሎችም እንዲያበራ ክርስቲያናዊ ምግባርም ከራስ ተርፎ ለሰዎች ዅሉ ደምቆ በአርአያነት ይታያልና፡፡ እኛም ‹‹ብርሃን ሳለላችሁ በብርሃን ተመላለሱ›› ተብሎ እንደ ተጻፈ የጽድቅ ሥራ የማይገኝበት ጊዜ የጨለማ ዘመን ከመምጣቱ በፊት የጽድቅ ሥራ መሥራት በምንችልበት ጊዜ ዅሉ በመልካም ምግባር ጸንተን እንኑር (ዮሐ. ፲፪፥፴፭-፴፮፤ ፩ኛ ዮሐ. ፩፥፯)፡፡

ደግሞም መልካም ግብር ያላቸው ምእመናን በብርሃን ይመሰላሉ፤ ብርሃን በግልጽ ለሰዉ ዅሉ እንደሚታይና እንደሚያበራ መልካም ምግባር ያላቸው ምእመናንም በጽድቅ ሥራቸው ለብዙዎች አርአያ፣ ምሳሌ ይኾናሉና፡፡ ‹‹እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ፡፡ በተራራ ላይ ያለች ከተማ ልትሠወር አይቻላትም›› እንዳለ ጌታችን በወንጌል (ማቴ. ፭፥፲፬)፡፡ እንግዲህ ዅላችንም በጨለማ ከሚመሰለው ኀጢአት ወጥተን በብርሃን ወደሚመሰለው የጽድቅ ሕይወት ተመልሰን በክርስቲያናዊ ምግባር በርተን እኛ በርተን ወይም ጸድቀን ለሌሎችም ብርሃን ማለትም የጽድቅ ምክንያት ልንኾን ይገባናል፡፡ ‹‹ብርሃናችሁ በሰዉ ዅሉ ፊት ይብራ›› ተብለን ታዝዘናልና (ማቴ. ፭፥፲፮)፡፡

በአጠቃላይ ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን፣ መዓልት የሚባለው ክፍለ ክረምት ‹‹ቡሄ ካለፈ የለም ክረምት፤ ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት›› እንደሚባለው ክረምቱ እየቀለለ፣ ማዕበሉ እየቀነሰ፣ ዝናሙ እያባራ፣ ሰማዩ እየጠራ የሚሔድበት የንጋት፣ የወጋገን፣ የብርሃን ጊዜ ነው፡፡ ልክ እንደ ዘመኑ እኛም እንደ ደመና በልባችን የቋጠርነውን ቂምና በቀል፤ እንደ ጨለማ በአእምሯችን የሣልነውን ክፋትና ኑፋቄ ወይም ክህደት፤ እንደ ዝናምና ማዕበል በወገን ላይ ያደረስነውን ጥፋትና በደል በንስሐ ፀሐይ አስወግደን ወደ ብርሃኑ ሕገ እግዚአብሔር፤ ወደ ብርሃኑ ኢየሱስ ክርስቶስ፤ ወደ ብርሃኑ ምግባረ ሠናይ፤ ወደ ብርሃኑ ክርስትና እንመለስ፡፡ እንዲህ እንድናደርግም ልዑል እግዚአብሔር ‹‹በሕይወታችሁ ውስጥ ብርሃን ይኹን!›› ይበለን፡፡ እርሱ ‹‹ብርሃን ይኹን›› ካለ የኀጢአት ጨለማ በእኛ ላይ ለመሠልጠን የሚችልበት ዓቅም አያገኝምና፡፡

ይቆየን

ዐውደ ርእዩ በኢንድያናፖሊስ ከተማ ቀረበ

በዝግጅት ክፍሉ

ነሐሴ ፲፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.

‹‹ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ›› በሚል ርእስ በማኅበረ ቅዱሳን የተዘጋጀው ልዩ ዐውደ ርእይ በአሜሪካ አገር በኢንዲያናፖሊስ ከተማ ለምእመናን ቀረበ፡፡

ዐውደ ርእዩ በአባቶች ቡራኬ ሲከፈት

በማኅበረ ቅዱሳን አሜሪካ ማእከል ኢንዲያና ግንኙነት ጣቢያ አዘጋጅነት ሐምሌ ፳፱ እና ፴ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም የቀረበው ይህ ልዩ ዐውደ ርእይ በጸሎተ ወንጌል ተባርኮ በወጣቶች እና ሕፃናት ዘማርያን ያሬዳዊ መዝሙሮች ከቀረቡ በኋላ ከኢንዲያና እና አጎራባች ግዛቶች በመጡ ከሦስት መቶ ስልሳ በላይ በሚኾኑ ካህናትና ምእመናን እንደ ተጐበኘ የአሜሪካ ማእከል አስታውቋል፡፡

የዐውደ ርእዩ ታዳሚዎች በከፊል

እንደ ማእከሉ ማብራሪያ የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ፣ ሐዋርያዊ አገልግሎቷ፣ ተጋድሎዋ፣ ያጋጠሟት ችግሮች እና ችግሮቿን ከመፍታት አንጻር የምእመናን ድርሻ እንደዚሁም የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት በቤተ ክርስቲያን የሚሉ ጉዳዮች በዐውደ ርእዩ የተካተቱ የትዕይንት ክፍሎች ሲኾኑ፣ ትዕይንቶቹም በአማርኛ፣ ትግርኛ እና እንግሊዝኛ ቋንቋዎች ተተርጕመው ለወጣቶች እና ሕፃናት በሚመጥን መልኩ ቀርበዋል፡፡

አባቶች ለምእመናን ጥያቄዎች ምላሽ ሲሰጡ

መልአከ ሰላም ቆሞስ አባ ኃይለ ማርያም የኢንዲያናፖሊስ ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ እና መልአከ ኃይል ቀሲስ ፍቅረ ኢየሱስ የኬንታኪ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ካህን ከሌሎች አባቶች ጋር በዐውደ ርእዩ ተገኝተው ከምእመናን ለሚነሡ ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት የአባትነት ድርሻቸውን ተወጥተዋል፡፡

የዐውደ ርእዩ ትዕይንቶች ወደ ትግርኛ ቋንቋ ተተርጕመው ለምእመናን እንዲቀርቡ በማድረግ በኢንዲያናፖሊስ ከተማ የሚኖሩ ትግርኛ ቋንቋ መናገር የሚችሉ ካህናት እና ምእመናን ድርሻ የላቀ እንደ ነበርም በማእከሉ ሪፖርት ተጠቅሷል፡፡

ወጣቶች እና ሕፃናት መዝሙር ሲያቀርቡ

በአጠቃላይ የዐውደ ርእዩ ዝግጅት ላይ የኢንዲያናፖሊስ ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ፣ የሰንበት ት/ቤቱ አባላት፣ የአጥቢያው ምእመናን፣ የኢንዲያና ግንኙነት ጣቢያ እና የቺካጎ ንዑስ ማእከል አባላት በገላጭነት፣ በአስተባባሪነት እና በልዩ ልዩ የአገልግሎት ዘርፎች ከፍተኛ ተሳትፎ አድርገዋል፡፡

በመጨረሻም የዝግጅት ኮሚቴው ሰብሳቢ ዶክተር በላይነህ ደስታ ለዝግጅቱ መሳካት ከፍተኛ አስተዋጽዖ ላደረጉ የቤተ ክርስቲያን አባቶች፣ ስፖንሰር (ድጋፍ) በማድረግ ለተባበሩ የግል ድርጅቶች እና ለበጎ አድራጊ ምእመናን ምስጋና ካቀረቡ በኋለ ዐውደ ርእዩ በአባቶች ጸሎት ተፈጽሟል፡፡

የድንግል ማርያም ክብሯ፣ ዕረፍቷ እና ትንሣኤዋ

 

በዲያቆን ታደለ ፈንታው

ነሐሴ ፲፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ክብሯ

እግዚአብሔር ዘላለማዊ ኀይሉንና አምላክነቱን ለዓለም ከገለጸበት ታላቅ ሥራ መካከል በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም የገለጸው ድንቅ ሥራው በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ቀዳሚውን ሥፍራ ይይዛል፡፡ ይህንን ኹኔታ ድንግል ማርያም ‹‹ብርቱ የኾነ እርሱ ታላቅ ሥራን በእኔ አድርጓል፤ ስለዚህም ፍጥረት ዅሉ ያመሰግኑኛል›› በማለት ገልጻዋለች (ሉቃ. ፩፥፵፱)፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ‹‹ከሴቶች መካከል ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ›› ብሏታል (ሉቃ. ፩፥፳፰)፡፡ ቅድስት ኤልሳቤጥም ‹‹የጌታዬ እናት›› ብላታለች (ሉቃ. ፩፥፵፫)፡፡ ቅዱስ ዳዊት ደግሞ ‹‹ልጄ›› ይላታል (መዝ. ፵፬፥፱)፡፡ ሰሎሞንም ‹‹እኅቴ›› ብሎ ጠርቷታል (መኃ. ፭፥፩)፡፡ ለወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ የተሰጠችውም እናት ኾና ነው (ዮሐ. ፲፱፥፳፮)፡፡

ቅዱስ እግዚአብሔር ፍጥረቱንና ዓለሙን ለማዳን የወሰነው ጊዜ ሲደርስ የተወለደው ከድንግል ማርያም ነው፡፡ አስቀድሞ በመልአኩ አፍ እንዳናገረ ክብሩ በእርሷ ላይ ታየ (ኢሳ. ፷፥፪)፡፡ ማኅፀኗን ከተማ አድርጎ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በእርስዋ አደረ፡፡ መንፈስ ቅዱስ በእመቤታችን ላይ የማደሩ ምሥጢር ያነጻቸው፤ ይቀድሳቸው፤ በሥጋም በነፍስም መርቶ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ያገባቸው ዘንድ በነቢያት፣ በሐዋርያት ላይ እንዳደረው ዓይነት አይደለም፡፡ ከሦስቱ አካል አንዱ አካል እግዚአብሔር ወልድ (ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ) ከሥጋዋ ሥጋን፣ ከነፍስዋ ነፍስን ነስቶ ፍጹም ሰው፣ ፍጹም አምላክ ኾነ እንጂ፡፡ ቅዱስ ሉቃስ ይህን ዘለዓለማዊ እውነት ‹‹መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፤ የልዑል ኃይልም ይጸልልሻል፡፡ ስለዚህ ከአንቺ የሚወለደው ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል›› በማለት ገልጾታል (ሉቃ. ፩፥፵፭)፡፡

‹‹በእግዚአብሔር፣ በመላእክትና በሰው ፊት የከበረ ሰው መታሰቢያው ለዘለዓለም ነው፡፡ በቤቱ በቅጥሩ የማይጠፋ የዘለዓለም ስምን ይቀበላልና›› ተብሎ በትንቢተ ኢሳይያስ እንደ ተገለጸው (ኢሳ. ፶፭፥፫) ይህን ታላቅ በረከት እንደሚሰጣቸው የተናገረው የማይዋሸው ቅዱስ እግዚአብሔር ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ወልድ እናት ከድንግል ማርያም የበለጠ በሰውና በእግዚአብሔር ዘንድ የከበረ ማንን ልንጠራ እንችላለን? እንደ እርሷስ ሊታሰብ፣ ሊከበርም የሚችል በቅድስና ሕይወት ያለፈ ማን ይኖራል? እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ስለ ድንግል ማርያም ያልተናገረበት ጊዜ፤ ያላናገረው ቅዱስም የለም፡፡

ቅዱስ አግናጥዮስ ዘአንጾኪያ ለኤፌሶን ክርስቲያኖች በጻፈው መልእክቱ እንደ ተናገረው ‹‹የቅድስት ማርያም ዘለዓለማዊ ድንግልና፤ አማኑኤልን መውለዷና የማይሞተው ጌታ መሞቱ›› እነዚህ ሦስቱ ከዚህ ዓለም ጥበበኞችና ገዢዎች የተሰወሩ ምሥጢራት ናቸው፡፡ ቅዱስ አግናጥዮስ ‹‹እነዚህ ድንቅ ምሥጢራት በራሳቸው ከንግግርና ከቋንቋዎች በላይ ኾነው የሚነገሩ በእግዚአብሔር የዝምታ መጐናጸፊያ የተጠቀለሉ ድብቅና ጣፋጭ ምሥጢሮች ናቸው›› ይላል፡፡ የእመቤታችን ክብር ውስንና ደካማ የኾነ አእምሮ ሊገነዘበው ከሚችለው በላይ ነውና፡፡ የእመቤታችን ምስጋናዋ የበዛለት ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊም ‹‹አቤቱ መሰንቆ ልቡናዬን አነቃቃ፤ የልቤንም እንዚራ፡፡ ድምፁን ከፍ አድርጎ የዳዊት ልጅ የኾነችውን፣ የጌታውን እናት ድንግል ማርያምን ያመሰግናት ዘንድ፤ ለዓለም ሕይወት የሚሰጠውን የወለደች እናቱ የኾነች እርሷን ከፍ ከፍ ያደርጋት ዘንድ›› ብሏል፡፡ በሌላም አንቀጽ ደግሞ ‹‹ከሕሊናት ዅሉ በላይ ለኾነ ለዚህ ነገር አንክሮ ይገባል፡፡ ምድራዊት ሴት ፈጣሪዋን ወለደችው፤ እርሱም እናቱን ፈጠረ›› በማለት የእመቤታችንን ወላዲተ አምላክነት ያደንቃል፡፡

ኢትዮጵያዊው ሊቅ ደራሲና ገጣሚ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም እንዲህ ሲል ክብሯን ገልጾታል፤ ‹‹የእስራኤል ንጉሥ በእስራኤል ልጅ አደረ፤ የዳዊት አምላክ ከዳዊት ልጅ ሥጋን ለበሰ፡፡ የዕብራውያን ጌታ በዕብራውያን ልጅ ማኅፀን ተወሰነ፡፡ ለአብርሃም የዕብራይስጥ ልሳን ያስተማረው ከቀድሞም ያልሰማውን ልሳን እንዲናገር አፉን ጆሮውን የከፈተለት ከዕብራዊት ድንግል ተወለደ፤ በድንግልና ወተት ጥቂት ጥቂት እያለ አደገ፡፡ የሕፃናትን ሥርዓት እንዳያጎድል አፉን የሚፈታባት ዘመን እስኪፈጸም ጥቂት ጥቂት እያለ በዕብራይስጥ ልሳን ሲናገር ኖረ፡፡ ለሙሴ በዕብራይስጥ ልሳን በጣቶቹ የተጻፉትን ዐሠርቱ ቃላትን የሰጠ የዕብራይስጥ ፊደል ለመማር ከመምህር እግር በታች ተቀመጠ፡፡ የባቢሎን አውራጃ በምትኾን ሰናዖርም የፍጥረትን ሁሉ ቋንቋ የበተነ እርሱ የአሕዛብን ቋንቋ እንደማያውቅ እናቱ አፍ በፈታችበት ልሳን በዕብራይስጥ ልሳን ሲናገር ኖረ፡፡ ጆሮ ይህንን ነገር ከመስማት የተነሣ የሚለመልምበት ይህ ነገር ዕፁብ ድንቅ ነው፡፡ ለዚህ አንክሮ ይገባል፡፡›› ይህ በሰው ጥበብ በብራናና በቀለም የተጻፈ እውነት ሳይኾን ለድኅነት በተጠሩ ሰዎች ዅሉ ልቡና በአምላክ ጥበብ የተጻፈ እውነት ነው፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ በማኅፀን የተጀመረው የማዳን ሥራ፤ ፍጻሜውን ያገኘው በቀራንዮ ነው፡፡ የጌታ ልደቱና ጥምቀቱ፣ ሞቱ ትንሣኤው፣ ዕርገቱና ዳግመኛ መምጣቱ በነገረ ድኅነት ትምህርታችን እጅግ ጠቃሚ የኾኑ ምሥጢራት ናቸው፡፡ ቤተልሔም የሥጋዌውን ምሥጢር ሲያሳይ ዮርዳኖስ ቀዳማዊ ልደቱን ያሳያል፡፡ የመጀመርያው የእኛ ባሕርይ ሲኾን ሁለተኛ የጌታ የራሱ የባሕርይ ገንዘቡ የኾነ ነው፡፡ እርሱ የሰው ልጅ ኾነ፤ እኛ ደግሞ የእግዚአብሔር ልጆች ኾንን፡፡ ይህ ዅሉ የተደረገው አምላካችን ከድንግል ማርያም በነሣው ሥጋ ነው፡፡ እርሱ የእኛን ተፈጥሮ ገንዘቡ ስላደረገ እኛ ደግሞ የእርሱን ቅድስና ገንዘብ በማድረግ የመንግሥቱ ተካፋዮች ኾንን፡፡ የእኛ የኾነው ዅሉ የእርሱ፤ የእርሱ የኾነውም የእኛ ኾነ፡፡ የእኛ መንፈሳዊ ልደት የተገኘው ጌታ በሥጋ ከቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደው ልደት ነው፡፡ የቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን አምላክና የሰው ልጆች የተገናኙበት፤ አምላክና ሰው የተዋሐዱበት መካነ ምሕረት ነው፡፡ እግዚአብሔር ዙፋኑን ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀናት የዘረጋበት መካነ ሰላም ነው፡፡ የእግዚአብሔር ዙፋን ፍጹም በማይናወጥና ጸጥታ በነገሠበት ሥፍራ የሚዘረጋ የክብር ዙፋን ነው፡፡ ይህም ዙፋን የቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን ነው፡፡ ለዚህ ክብር በቅታ ያከበረችንን፤ ከእግዚአብሔር ጋር ያዛመደችንን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን እንደምን አናከብራትም?

ዕረፍቷ

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በአባት በእናቷ ቤት ሦስት ዓመት፤ በቤተ መቅደስ ዐሥራ ሁለት ዓመት፤ ከልጇ ጋር ሠላሳ ሦስት ዓመት ከሦስት ወራት፤ ከጌታ ስቅለት በኋላ ዐሥራ አምስት ዓመታት ኖራለች፡፡ ጌታን የፀነሰችበትን ወራት ስንጨምር እመቤታችን በዚህ ዓለም በሥጋ የቆየችበት ጊዜ ስድሳ አራት ዓመት ይኾናል፡፡ ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ ያረፈችውም በጥር ሃያ አንድ ቀን ነው፡፡ ኢትዮጵያዊው ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በመጽሐፈ አርጋኖን ድርሰቱ ‹‹ከሚያሰጥመው ባሕር ሞገድ የተነሣ የማትነቀነቅ፤ መልሕቆቿም በሦስቱ ሥላሴ ገመድ የተሸረቡ ናቸው፡፡ ይህቺ ደግሞ ከነፋሳት ኀይል የተነሣ የማትናወጥ፤ በጭንጫ ላይ ያለች የዕንቈ ባሕርይ ምሰሶ ናት፡፡ እርሷን የተጠጋ መውደቅ መሰናከል የለበትም›› የሚላት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሞት አይቀርምና እርሷም እንደሰው የምትሞትበት ጊዜ ደረሰ፡፡ እግዚአብሔር አያዳላምና (ሮሜ. ፪፥፲፩)፡፡

የቤተ ክርስቲያን ትውፊት የድንግል ማርያም ሞት በሚከተሉት ምክንያቶች እንደ ኾነ ያስረዳል፤ የመጀመሪያው፡- ‹‹ለመለኮት ማደርያ ለመኾን የበቃችው ኀይል አርያማዊት ብትኾን ነው እንጂ ምድራዊት ሴትማ እንደምን ሰማይና ምድር የማይችለውን ልትሸከመው ይቻላታል?›› የሚሉ ወገኖች ነበሩና በእርግጥም እግዚአብሔር ወልድ የተዋሐደው የሰው ልጆችን ሥጋ እንጂ የመላእክትን አለመኾኑን ለማጠየቅ ነው፡፡ ጌታችን የሱራፌልን፣ የኪሩቤልን ባሕርይ ባሕርዩ አላደረገም፡፡ የመላእክትንም ባሕርይ እንደዚሁ፡፡ የእርሷን አካል ባሕርዩ አደረገ እንጂ፡፡ ይህንንም ቅዱስ ጳውሎስ ሲያስረዳ ‹‹… የአብርሃምን ዘር ይዟል እንጂ የያዘው የመላእክትን አይደለም›› አለ (ዕብ. ፪፥፲፬-፲፭)፡፡ በዚህም ድንግል ማርያም የአዳም ዘር መኾኗ ታወቀ፡፡ ሁለተኛው፡- ቅዱስ ያሬድ እንደ ተናገረው ጌታችን በፍርዱ አድልዎ የሌለበት አምላክ መኾኑ ይታወቅ ዘንድ ነው፡፡ ሥጋ የለበሰ ዅሉ በለበሰው ሥጋ ሞትን ይቀምስ ዘንድ የግድ ነውና፡፡

በቅዱሳት መጻሕፍት ሞትን እንዳያዩ የተወሰዱ ቅዱሳን ሄኖክ፣ ኤልያስ፣ ሌሎችም እንዳሉ ተጠቅሷል፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያም የኀያሉ እግዚአብሔር እናቱ፣ መቅደሱ፣ ታቦቱ፣ መንበሩ ኾና እያለ ሞትን መቅመሷ የሚያስገርም ምሥጢር ነው፡፡ ይህ ከሕሊናት ዅሉ በላይ የኾነው ምሥጢር ርቀቱ (ረቂቅነቱ) በሊቃውንት እንዲህ ተገልጿል፤ ‹‹ለምንት ይዜኃር ኃያል በኃይሉ ወባዕል በብዝኃ ብዕሉ ኢያድለወ ሞተ ክርስቶስ ለሥጋ አባሉ ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ ሞታ ለማርያም የዐጽብ ለኵሉ፤ ኀይለኛ በኀይሉ ለምን ይታጀራል? ባለ ጸጋም በሀብቱ ብዛት፡፡ ክርስቶስ ለአካሉ አላዳላም፤ ሞትስ ለሟች ይገባዋል የእመቤታችን የቅድስት ማርያም ሞት ግን አስደናቂ ነው፡፡››

ትንሣኤዋ

ለአምላካችን ለልዑል እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይግባውና ከሞት ወጥመድ በላይ እንኳን የኾነ ሌላ ኀይል አለ፤ ይኼውም ሞት ፈጽሞ ሊያሸንፈውና ሊገዳደረው የማይችል የእግዚአብሔር መለኮታዊ ኀይል ነው፡፡ በሰይጣን ዘንድ ያለው የሞት ኀይል ነው፡፡ ሕያው እግዚአብሔር የሕያዋን አምላክ ነውና ሞት ሊያሸንፈው ሊደርስበትም የማይችለውን ሕይወት ይሰጣል፡፡ ይህንን እግዚአብሔር የሚሰጠውን ሕይወት ሰይጣን በእጁ ሊነካው ከቶውንም አይችልም፡፡ እግዚአብሔር ለሙታን ሕይወትን ይሰጣል፡፡ የሞትም የሕይወትም ባለቤት እርሱ ነውና፡፡ ከሞት ኀይል በላይ የኾነው ይኸው የእግዚአብሔር መለኮታዊ ሥልጣን የድንግል ማርያምን ሥጋ መልካምም ኾነ ክፉ ለሠሩ ሰዎች ዋጋ ይከፍል ዘንድ ለፍርድ እስከሚመጣበት ጊዜ ድረስ በመቃብር ውስጥ ተጠብቆ እንዲቆይ፤ ፈርሶና በስብሶ በምድር ላይ እንዲቀር አላደረገም፡፡ ከሙታን መካከል ተለይታ ተነሥታለች፡፡ ሊቁ ‹‹ለዛቲ ብእሲት ሠረቀ ላዕሌሃ ብዕለ ጸጋሁ ለአብ ወአግዓዛ እምእኩይ ውስተ ሠናይ እሞት ውስተ ሕይወት፤ በድንግል ማርያም ላይ የአብ የባለጸግነቱ ብዛት ተገለጠ፤ ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከክፉ ዓለም ወደ በጎ ዓለም አሸጋግሯታልና›› በማለት ያቀረበው ምስጋናም ትንሣኤዋን የሚገልጽ ነው፡፡

መንፈስ ቅዱስ በድንግልና ፀንሳ በድንግልና መውለዷን በትንቢት እንዳናገረ ትንሣኤዋንም በትንቢት ሲያናግር ኑሯል፡፡ ይህን ታላቅ ምሥጢር ቅዱስ ዳዊት ‹‹ተንሥእ እግዚኦ ውስተ ዕረፍትከ አንተ ወታቦተ መቅደስከ፤ አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፤ አንተና የመቅደስህ ታቦትም›› ብሎ ገልጾታል (መዝ. ፻፴፩፥፰)፡፡ ነቢዩ የትንቢት ክፍል ትንሣኤዋን አስረድቷል፡፡ ታቦት የጽላቱ ማደሪያ ነው፡፡ በታቦቱ ውስጥ የሚያድረው በእግዚአብሔር ጣቶች የተጻፈው ሕጉ ነው፡፡ ይህ እግዚአብሔር ያከበረው ነገር ኾኖ ሊመጣ ላለው ነገር ማሳያ ነው፡፡ እውነተኛዋ ታቦት ድንግል ማርያም ናት፡፡ ሙሴ በተቀበለው ታቦት ውስጥ ያለው ጽላት በውስጡ የያዘው ሕጉን ነው፤ በድንግል ማርያም ላይ ያደረው ግን የሕጉ ባለቤት ነውና፡፡

እመቤታችን ከጌታችን ፅንሰት ጀምሮ እስከ ቀራንዮ አደባባይ ድረስ፤ ሐዋርያት ጉባኤያትን ሲያካሒዱ አብራ ነበረች፡፡ ይህ ዅሉ ታላቅ ሥራ ከተፈጸመ በኋላ ዓረፍተ ዘመን ገታት፡፡ በሥጋ ዐረፈች፡፡ ሐዋርያት ሊቀብሯት ሲሹም ከአይሁድ ክፋት የተነሣ ልጇ ሌላ ክብርን ደረበላት፡፡ ከጌቴሴማኒ ሥጋዋ ተነጥቆ በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር እስከ ነሐሴ ዐሥራ ስድስት ቀን ለሁለት መቶ አምስት ቀናት ቆይቷል፡፡ ልጇ ወዳጇ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን በሥልጣኑ እንዳሸነፈ የልጇ መለኮታዊ ኀይል ሞትን አሸንፋ እንድትነሣ አደረጋት፤ ጠቢቡ ሰሎሞን ስለ ትንሣኤዋ የተናገረው ቃል ተፈጸመ፡፡ ጠቢቡ ‹‹ወዳጄ ሆይ ተነሺ፤ ውበቴ ሆይ ነይ፡፡ እነሆ ክረምት አለፈ፤ ዝናሙም አልፎ ሔደ፡፡ አበቦች በምድር ላይ ተገለጡ፤ የዜማም ጊዜ ደረሰ፡፡ የቁርዬም ቃል በምድር ላይ ተሰማ፤›› (መኃ. ፪፥፲-፲፬) በማለት የተናገረው ትንቢት የዚህ ዓለም ድካሟ ዅሉ መፈጸሙን ያስረዳል፡፡

እመቤታችን ልጇን ይዛ ከአገር አገር በረሀብና ጥም የተንከራተተችበት ጊዜ አሁን አለፈ፡፡ ታናሽ ብላቴና ሳለች ልጇን አዝላ በግብጽ በረኀ የተቀበለችው መከራ ዅሉ ፍጻሜ አገኘ፡፡ ከእግረ መስቀል ሥር ወድቃ የልጇን የቆሰለ ገላ እየተመለከተች የደረሰባት ልብ የሚሰነጥቅ ሐዘን ወደ ደስታ ተለወጠ፡፡ ‹‹በነፍሷ ሰይፍ ያልፋል›› ተብሎ የተነገረው ልብ የሚሰነጥቅ መከራ እንደ ነቢዩ ቃለ ትንቢት የሚቀጥልበት ጊዜ ተፈጸመ፡፡ እርሷ ባለችበት ሥፍራ የሕይወት ትንሣኤ ያላቸው ሰዎች ይኾኑ ዘንድ አስቀድማ ከሙታን ተለይታ በመነሣት የተጠበቀልን ተስፋ ማሳያ ኾነችን፡፡ በእግዚአብሔር መንግሥት ስደት፣ መከራ፣ ሐዘን፣ ሰቆቃ የለም፤ መገፋት መግፋትም የለም፡፡ ከእንግዲህ ወዲያ ልጇ ሲንገላታ፣ ሲሰደድ ሲገረፍ፣ ሲሰቀል፣ ሲቸነከር ያየችበት ዓለም አለፈ፡፡ አሁን የልጇን ልዕልና ከሚያደንቁ ጋር ታደንቃለች፤ ከፍ ከፍ ከሚያደርጉት ጋር ታከብረዋለች፡፡ ይኸውም ከገቡ የማይወጡበት፤ ሐዘን፣ መከራ፣ ችግር የሌለበት ሰማያዊት አገር ነው፡፡ ቅዱሳን ሩጫቸውን ጨርሰው የድል አክሊልን የሚቀዳጁበት ሥፍራ ነው፡፡ በዚያም ከፍጡራን ዅሉ ከፍ ባለ በታላቅ ክብርና ጸጋ ለዘላለም ትኖራለች፡፡

ልመናዋ፣ ክብሯ፣ ፍቅሯ፣ አማላጅነቷ፣ የልጇም ቸርነት በዅላችንም ላይ አድሮ ይኑር፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

‹‹አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፤ አንተና የመቅደስህ ታቦትም›› (መዝ. ፻፴፩፥፰)

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

ነሐሴ ፲፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

እግዚአብሔር አምላካችን ‹‹አምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ ስደትህን በስደቴ፣ ሞትህን በሞቴ አጥፍቼ፤ የቀደመ ክብርህን መልሼ ያጣኸውን ርስት፣ ገነትን (መንግሥተ ሰማያትን) አወርስሃለሁ›› በማለት ለአባታችን አዳም የገባው ቃል ኪዳን ፍጻሜው በደረሰ ጊዜ ለእግዚአብሔር ወልድ ማደሪያነት የተመረጠች፣ ለአዳም እና ለዘሩ መዳን ምክንያት የኾነች ‹‹የልጅ ልጅ›› የተባለችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዳ ፲፭ ዓመት ሲኾናት በቅዱስ ገብርኤል ብሥራት የእግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ ማደሪያ ኾነች (ገላ. ፬፥፬)፡፡ ልጇን በወለደች ወቅት ‹‹የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት አለ?›› የሚለውን የሰብአ ሰገልን ዜና የሰማው ሄሮድስ ሕፃኑን ለመግደል ፈለገ፡፡ እመቤታችንም ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስን ለማዳን ወደ ግብጽ ይዛው ተሰደደች (ማቴ. ፪፥፲፪)፡፡ የስደቱ ዘመን አልቆ ወደ ኢየሩሳሌም ከተመለሱ በኋላም ኢየሱስ ክርስቶስ ፴ ዓመት ሲኾነው ስለ መንግሥተ ሰማያትና ስለ ሰው ልጆች ነጻነት ይሰብክ ጀመር፡፡ ከዚህ በኋላ የአዳምና የዘሩን ሞት ለማጥፋት በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ሞተ፤ በሦስተኛው ቀን ተነሥቶ፣ ባርነትን አስወግዶ ለሰው ልጅ ነጻነትን ዐወጀ፡፡

በዚህ ዅሉ የድኅነት ጉዞ ውስጥ ያልተለየችና ምክንያተ ድኂን የኾነችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደች በ፷፬ ዓመቷ ጥር ፳፩ ቀን ዐርፋለች፡፡ ይህን የእመቤታችን ሞት የሚያስደንቅ መኾኑን ታላቁ የቤተ ክርስቲያናችን አባት ቅዱስ ያሬድ «ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ ሞታ ለማርያም የዐጽብ ለኵሉ፤ ሞት ለማናቸውም ሰው የተገባ ነው፡፡ የማርያም ሞት ግን ዅሉን ያስደንቃል» በማለት ገልጾታል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት የእመቤታችንን የከበረ ሥጋዋን ገንዘውና ከፍነው ለማሳረፍ ወደ ጌቴሴማኒ መካነ ዕረፍት (የመቃብር ቦታ) ይዘው ሲሔዱ አይሁድ በቅናት መንፈስ ተነሣሥተው «ቀድሞ ልጇንበሦስተኛው ቀን ከሙታን ተነሣ፤ በዐርባኛው ቀን ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ እንደገናም ተመልሶ ይህን ዓለም ለማሳለፍ ይመጣልእያሉ ሲያውኩን ይኖራሉ፡፡ አሁን ደግሞ እርሷንምእንደ ልጇ ተነሣች፣ ዐረገችእያሉ ሲያውኩን ሊኖሩ አይደለምን? ! ተሰብሰቡና በእሳት እናቃጥላት» ብለው ተማከሩ፡፡

ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊም የከበረ ሥጋዋን የተሸከሙበትን አጎበር (የአልጋ ሸንኮር) በድፍረት ያዘ፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ በእሳት ሰይፍ ሁለት እጆቹን ቆረጣቸው፡፡ እጆቹ ተንጠልጥለው ከቆዩ በኋላ ‹‹በእውነት የአምላክ እናት ናት›› ብሎ ስለ አመነ እጆቹ ተመልሰው እንደ ነበሩ ኾነዉለታል፡፡ ከዚህ በኋላ መልአከ እግዚአብሔር የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ  ከሐዋርያው ዮሐንስ ጋር ነጥቆ ወስዶ በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አስቀመጠው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ከጥቂት ወደ ሐዋርያት በተመለሰ ጊዜም የእመቤታችን የከበረ ሥጋ በገነት መኖሩን ነገራቸው፡፡ ሐዋርያትም የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ አግኝተው  ለመቅበር በነበራቸው ምኞትና ጉጉት ‹‹ዮሐንስ አይቶ እኛ እንዴት ሳናይ እንቀራለን? ብንጠየቅስ ምን እንመልሳለን?›› በማለት በነሐሴ አንድ ቀን ሱባኤ ጀምረው ሲጾሙና ሲጸልዩ ከሰነበቱ በኋላ በሁለተኛው ሱባዔ መጨረሻ (ነሐሴ ፲፬ ቀን) ጌታችን የእመቤታችንን ትኩስ የከበረ ሥጋ አምጥቶ ሰጥቷቸው በታላቅ ዝማሬና ውዳሴ በጌቴሴማኒ ቀብረውታል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ የእመቤታችን የቀብር ሥነ ሥርዐት ሲፈጸም አልነበረምና ከሀገረ ስብከቱ በደመና ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመጣ እመቤታችን በተቀበረች በሦስተኛው ቀን  እንደ ልጇ ተነሥታ ስታርግ አገኛት፡፡ በዚህ ጊዜ ‹‹ቀድሞ የልጅሽን፣ አሁን ደግሞ የአንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ›› ብሎ ቢያዝን እመቤታችን ከእርሱ በቀር ሌሎች ሐዋርያት ትንሣኤዋን እንዳላዩ ነግራ አጽናናችው፡፡ ወደ ምድር ወርዶ የኾነውን ዅሉ ለሐዋርያት እንዲነግራቸው አዝዛው፣ ለምልክት ይኾነው ዘንድም የተገነዘችበትን ሰበኗን ሰጥታው ወደ ሰማይ ዐርጋለች፡፡ ቅዱስ ቶማስም ሐዋርያት ወደ አሉበት ኢየሩሳሌም በደረሰ ጊዜ «የእመቤታችን ነገር እነዴት ኾነ  ብሎ ቢጠይቃቸው፤ «እመቤታችንን እኮ ቀበርናት» ብለው ነገሩት፡፡

እርሱም ምሥጢሩን ደብቆ «አይደረግም! ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር  እንደምን ይኾናል አላቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ‹‹አንተ መጠራጠር ልማድህ ነው፡፡ ቀድሞ የጌታን ትንሣኤ ተጠራጠርክ አሁንም አታምንም?›› ብሎ የእመቤታችን መካነ መቃብር ሊያሳዩት ይዘውት ሔዱ፡፡ መቃብሩን ቢከፍቱ የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ አጡት፤ ደነገጡም፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ቶማስ «አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ተነሥታ ዐርጋለች» ብሎ  የኾነውን ዅሉ ተረከላቸውና የሰጠችውን ሰበኗን አሳያቸው፡፡ እነርሱም ማረጓን አምነው ሰበኗን ለበረከት ተከፋፍለው ወደየአህጉረ ስብከታቸው ሔዱ፡፡ በዚያም ሕሙማንን ሲፈውሱበትና ገቢረ ተአምር ሲያደርጉበት ኖረዋል፡፡

በዓመቱ ‹‹ቶማስ ትንሣኤዋን አይቶ እንዴት እኛ ይቅርብን?›› ብለው ከነሐሴ ፩ ቀን ጀምሮ ሱባዔ ገብተው ነሐሴ ፲፮ ቀን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልመናቸውን ተቀብሎ እመቤታችንን መንበር፣ ቅዱስ ጴጥሮስን ንፍቅ (ረዳት) ቄስ፣ ቅዱስ እስጢፋኖስን ገባሬ ሠናይ (ዋና) ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ አቍርቧቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ እመቤታችንን ሐዋርያት በግልጽ እያዩዋት ከጌታችን ጋር በክብር በይባቤና በዝማሬ ወደ ሰማይ ዐርጋለች፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ትንሣኤ ጊዜያዊና ዘለዓለማዊ በመባል ይታወቃል፡፡ ጊዜያዊ ትንሣኤ የሚባለው የእግዚአብሔር ከሃሊነት የሚገለጽበት ተአምራዊ ሥራ ኾኖ በተወሰኑ ሰዎች ላይ የሚፈጸምና ዳግም ሞትን የሚያስከትል ነው፡፡ ለምሳሌ ኤልያስ ያስነሣውን ወልደ መበለት (፩ኛነገ. ፲፯፥፰-፳፬)፤ ዐፅመ ኤልሳዕ ያስነሣውን ሰው (፪ኛነገ. ፲፫፥፳-፳፩)፤ ወለተ ኢያኢሮስን (ማቴ. ፱፥፰-፳፮)፤ በዕለተ ስቅለት ከመቃብር ወጥተው በቅድስት ከተማ የታዩ ሙታንን (ማቴ. ፳፯፥፶፪-፶፫)፤ በቅዱስ ጴጥሮስ ጸሎትና ምልጃ የተነሣችዋን ጣቢታን (ሐዋ. ፱፥፴፮-፵፩)፤ እንደዚሁም ትንሣኤ አልዓዛርን መጥቀስ ይቻላል (ዮሐ. ፲፩፥፵፫-፵፬)፡፡ እነዚህ ዅሉ ለጊዜው ከሞት ቢነሡም ተመልሰው ዐርፈዋል፡፡ ወደፊትም ትንሣኤ ዘጉባኤ ይጠብቃቸዋል፡፡

ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት በትንቢቱ «ተንሥእ እግዚኦ ውስተ ዕረፍትከ አንተ ወታቦተ መቅድስከ፤ አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፤ አንተና የመቅደስህ ታቦትም» (መዝ. ፻፴፩፥፰) በማለት አስቀድሞ የክርስቶስን ትንሣኤ ከገለጸ በኋላ ቀጥሎ የመቅደሱ ታቦት እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም ከሞት እንደምትነሣ ተናግሯል (ማቴ. ፭፥፴፭፤ ገላ. ፬፥፳፮፤ ዕብ. ፲፪፥፳፪፤ ራእ.፫፥፲፪)፡፡ የቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ የክብርና የሕይወት ትንሣኤ ሲኾን ሁለተኛ ሞትን አያስከትልም፤ ትንሣኤ ዘጉባኤንም አይጠብቅም፡፡ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤያችን በኵር ኾኖ በሞተ በሦስተኛው  ቀን ተነሥቷል፡፡ እመቤታችንም በልጇ ሥልጣን፤  እንደ ልጇ ትንሣኤ በሦስተኛው ቀን ተነሥታ ትንሣኤ ዘጉባኤን ሳትጠብቅ በክብር ዐርጋለች፡፡

እንደዚህ ያለውን ትንሣኤ ከእርሷ በቀር ሌሎች ቅዱሳን ወይም ነቢያትና ሐዋርያት አላገኙትም፡፡ በዚህም ኹኔታ የቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ ከማናቸውም ትንሣኤ ልዩ ኾኖ እናገኘዋለን፡፡ ይህም ትንሣኤ ዘለዓለማዊ፣ ከዳግም ሞተ ሥጋ ነጻ የኾነ ትንሣኤ ነው፡፡ ዕርገቷም በመጽሐፍ ቅዱስ ከተገለጸው ከእነ ሄኖክና ኤልያስ ዕርገት የተለየ ነው፡፡ «ሄኖክ ሞትን እንዳያይ በእምነት ተወሰደ፤ እግዚአብሔርም ስለ ወሰደው አልተገኘም» ተብሎ እንደ ተጸፈ (ዕብ. ፲፩፥፭)፣ ሄኖክ ወደ ሰማይ ያረገው በምድር ሳለ እግዚአብሔርን በእምነቱና በመልካም ሥራው ስላስደስተና በሥራውም ቅዱስ ኾኖ ስለ ተገኘ ነው፡፡ ኾኖም ግን ወደፊትም ገና ሞት ይጠብቀዋል፤ ሞቶም ትንሣኤ ዘጉባኤ ያስፈልገዋል፡፡ ነቢዩ ኤልያስም በእሳት ሠረገላም ቢነጠቅም (፪ኛ ነገ. ፪፥፲) ወደፊት ሞት ይጠብቀዋል፤ ትንሣኤ ዘጉባኤም ያስፈልገዋል፡፡ የእመቤታችን ትንሣኤ ግን ሞት የሌለበት ዘለዓለማዊ ትንሣኤ ነው፡፡

በአጠቃላይ ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ በድርሰቱ ‹‹በቃልዋ የታመነች፣ በሥራዋም የተወደደች ቅድስት ድንግል ማርያምን መላእክት እያመሰገኗትና በመንፈሳዊ ደስታ እያጀቧት ወደ ሰማይ አሳረጓት›› ሲል እንደ ገለጸው፣ በመጽሐፈ ስንክሳርም እንደ ተመዘገበው ቅዱስ ዳዊት ‹‹በወርቅ ልብስ ተጐናጽፋ፣ ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች›› (መዝ. ፵፬፥፱) በማለት የተናገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ አባቷ ዳዊት በበገና፣ ነቢዩ ዕዝራ በመሰንቆው እያመሰገኗት፤ በቅዱሳን መላእክት፣ በቅዱሳን ነቢያትና ጻድቃን ዝማሬ በብሩህ ደመና ወደ ሰማይ ዐርጋ በክብር ተቀምጣለች፡፡ «እመቤታችን ድንግል ማርያም ከምድር ወደ ሰማይ ዐረገች፤ በሰማይም ከልጇ ጋር በአብና በመንፈስ ቅዱስ ቀኝ ተቀመጠች» እንዳለ ቅዱስ ያሬድ በመዝሙሩ፡፡ በዚያም ሥፍራ ሁለተኛ ሞት ወይም ኀዘን፣ ጩኸትና፣ ስቃይ የለም፡፡ የቀደመው ሥርዐት አልፏልና (ራእ. ፳፩፥፬-፭)፡፡

ስለዚህም የእመቤታችን ዕረፍቷ፣ ትንሣኤዋና ዕርገቷ በሚታሰብበት በጾመ ፍልሰታ ሳምንታት ምእመናንን ከአካባቢያቸው ራቅ ብለው በተለያዩ ገዳማትና አድባራት በመሔድ አለዚያም በየአጥቢያቸው በመሰባሰብ እመቤታችን በተለያዩ ጊዜያት ሞቷንና ትንሣኤዋን ለሐዋርያት የገለጸችበትን ኹኔታ ያስባሉ፡፡ በጾም በጸሎት ተወስነው የልጇን ቸርነት የድንግልን አማላጅነት በእምነት ኾነው ይማጸናሉ፡፡ እንደዚሁም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነሐሴ ፲፮ ቀን እናቱን መንበር፣ ቅዱስ ጴጥሮስን ተራዳዒ ካህን፣ ቅዱስ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ ሐዋርያትንም እመቤታችንንም ማቍረቡን በማሰብና ድኅት ሥጋ ድኅነተ ነፍስ ለማግኘት ቅዱስ ሥጋውን፣ ክቡር ደሙን ይቀበላሉ፡፡ ሱባዔው ሲፈጸምም «በእውነት ተነሥታለች» እያሉ በደስታ የጾሙን ወቅት ይፈጽማሉ፡፡ የእመቤታችን አማላጅነት፣ የትንሣኤያችን በኵር የኾነው የአምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቸርነት ከዅላችን ጋር ይኹን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

እግዚአብሔር በደብረ ታቦር

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፲፬ ቀን ፳፻፱ .

‹እግዚአብሔር› የሚለው ቃል ሦስቱም አካላት (አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ) በጋራ የሚጠሩበት መለኮታዊ ስያሜ ነው፡፡ ‹‹አንሰ ሶበ እቤ እግዚአብሔር እብል በእንተ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ከመ በአሐዱ ስም ሥሉሰ ያምልኩ፤ እኔእግዚአብሔር› በአልኹ ጊዜ ስለ አብም፣ ስለ ወልድም፣ ስለ መንፈስ ቅዱስም እናገራለሁ፡፡ (ምእመናን) በአንዱ ስም (በእግዚአብሔር) ሦስቱ አካላትን ያመልኩ ዘንድ›› እንዳለ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ነባቤ መለኮት (ሃይማኖተ አበው)፡፡

ቅዱሳት መጻሕፍት እንደሚነግሩን እግዚአብሔር አምላካችን በብሉይም ኾነ በሐዲስ ኪዳን በአንድነቱም በሦስትነቱም በግብር (በሥራ)፣ በራእይ፣ በገቢረ ተአምራትና በልዩ ልዩ መንገድ ለፍጡራኑ ተገልጧል፡፡ በብሉይ ኪዳን በቅዱሳን ነቢያትና በመሳፍንት፣ በነገሥታት፣ በካህናትና በነቢያት ላይ በማደር፤ በጻድቃኑ ላይ ቸርነቱን፣ በክፉ አድራጊዎች ላይ ደግሞ መቅሠፍቱን በመላክ በልዩ ልዩ ምልክትና በተአምራት ይገለጥ ነበር፡፡ በሐዲስ ኪዳን ደግሞ ለአዳምና ለልጆቹ በገባው ቃል መሠረት የሰውን ሥጋ ለብሶ፣ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ በአካለ ሥጋ ተገልጦ በገቢረ ተአምራቱ፣ በትንሣኤውና በዕርገቱ አምላክነቱን አሳይቷል፡፡ የብሉይ ኪዳኑ መገለጥ በምልክት፣ በራእይ፣ በድምፅና በመሳሰሉት መንገዶች የተደረገ መገለጥ ነበር፤ የሐዲስ ኪዳኑ ግን አምላካችንን በዓይነ ሥጋ ያየንበት መገለጥ ስለ ኾነ ከዅሉም የተለየ ጥልቅ ምሥጢር አለው፡፡ ‹‹መቼም ቢኾን እግዚአብሔርን ያየው አንድ ስንኳ የለም፤ በአባቱ እቅፍ ያለ አንድ ልጁ እርሱ ተረከው›› (ዮሐ. ፩፥፲፰) በማለት ወንጌላዊው ዮሐንስ እንደ ገለጸው፡፡

እግዚአብሔር በሐዲስ ኪዳን ያደረዉን መገለጥ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ከምሥጢረ ሥላሴ ጋር በሚያያዙ ሦስት ዐበይት መንገዶች ይገልጹታል፡፡ ይኸውም በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ በዮርዳኖስና በደብረ ታቦር ላይ እንደ ኾነ ያስረዳሉ፡፡ ‹‹በላዕሌኪ ወበዮርዳኖስ ወበታቦር ሥልሰ ጊዜያተ ዘአልቦ ተውሳከ ወአልቦ ሕጸተ ለውሉደ ሰብእ ያርኢ ዘሥላሴሁ ገጻተ ጽጌኪ ድንግል ተአምሪሁ ከሠተ ወበፀዳሉ አብርሀ ጽልመተ›› እንዳለ ደራሲ (ማኅሌተ ጽጌ)፡፡ ትርጕሙም እግዚአብሔር አምላክ ጭማሬም ጉድለትም የሌለበት ሦስትነቱን ለሰው ልጅ ያሳይ ዘንድ በእመቤታችን፣ በዮርዳኖስ እና በታቦር ሦስት ጊዜ ተአምራቱንና ምሥጢረ መለኮቱን መግለጡን፤ በብርሃነ መለኮቱም ጨለማውን ዓለም ብርሃን ማድረጉን ያስረዳል፡፡ ይህም ጌታችን በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን ተወስኖ ሲወለድ፤ እንደዚሁም በዮርዳኖስ ወንዝ በተጠመቀበት ዕለት እግዚአብሔር አብ ‹‹የምወደው ልጄ እርሱ ነው፤ እርሱን ስሙት›› ብሎ  ሲመሰክር፣ መንፈስ ቅዱስም በርግብ አምሳል ወርዶ በራሱ ላይ ሲያርፍ፤ በተመሳሳይ መልኩ በደብረ ታቦር ብርሃነ መለኮቱን ሲገልጥ መለኮታዊ አንድነቱና አካላዊ ሦስትነቱ መታወቁን ያመለክታል፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን የምናቀርበው ትምህርትም እግዚአብሔር በደብረ ታቦር የመገለጡን ምሥጢር የተመለከተ ነው፡፡ መልካም ንባብ!

በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈው ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተስእሎተ ቂሣርያ በዋለ በስድስተኛው ቀን ማለትም ሐዋርያት ሰዎች ክርስቶስን ማን እንደሚሉት በተናገሩ፤ ቅዱስ ጴጥሮስም ክርስቶስ የባሕርይ አምላክ መኾኑን በመሰከረ በሳምንቱ (ነሐሴ ፲፫) ምሥጢረ መለኮቱን ይገልጥላቸው ዘንድ ጌታችን ሦስቱን ደቀ መዛሙርት መርጦ ወደ ረጅም ተራራ ይዟቸው ወጥቷል (ማቴ. ፲፯፥፩)፡፡ ይህ ተራራ ታቦር መኾኑንም ሐዋርያት በሲኖዶሳቸው ጠቅሰውታል፡፡ ሊቀ ነቢያት ሙሴ ከመቃብር ወጥቶ፤ ነቢዩ ኤልያስም ከብሔረ ሕያዋን መጥቶ በተገኙበት ጌታችን በተወለደ በ፴፪ ዓመት ከ፯ ወር ከ፲፭ ቀኑ፣ በዘመነ ማቴዎስ፣ ነሐሴ ፲፫ ቀን በዕለተ እሑድ በዚህ ተራራ ምሥጢረ መለኮቱን ገልጧል፡፡ (መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ በመ/ አፈወርቅ ተክሌ፣ አዲስ አበባ፣ ፳፻፭ ዓ.ም፤ ገጽ ፫፻፲፬፫፻፲፯ እና ፬፻፩)፡፡

የጌታችን ብርሃነ መለኮቱ ሲገለጥም ፊቱ እንደ ፀሐይ አበራ፤ ልብሱም ነጭ ኾነ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው፡፡ አንዱን ለአንተ፣ አንዱን፣ ለሙሴ አንዱን ለኤልያስ ሦስት ዳስ እንሥራ›› እያለ ተማጸነ፡፡ እንዲህ ማለቱም ጌታችን በተአምራቱ ሲራቡ እያበላቸው፣ ሲጠሙ እያጠጣቸው፣ ሲታመሙ እየፈወሳቸው፣ ቢሞቱ እያነሣቸው፤ ሙሴም እንደ ቀድሞው ደመና እየጋረደ፣ መና እያወረደ፣ ባሕር እየከፈለ፣ ጠላትን እየገደለ፤ ኤልያስ ደግሞ ሰማይን እየለጎመ፣ እሳት እያዘነመ፣ ዝናም እያቆመ አብረው በደብረ ታቦር እንዲኖሩ የነበረዉን መሻት ያመላክታል፡፡ የራሱን የሐዋርያትን ሳያነሣ የነቢያትን ስም መጥቀሱም በአንድ በኩል ትሕትናውንና ጌታችን አብሮ ያኖረኛል ብሎ ተስፋ ማድረጉን፤ በሌላ በኩል ደግሞ የክርስቶስን አምላክነት በሚገባ አለመረዳቱን ያመላክታል፡፡ ጌታችንን በተራራ ላይ በሰው ሠራሽ ቤት ይኖር ዘንድ ጠይቆታልና (ትርጓሜ ወንጌለ ማቴዎስ)፡፡

አምላከ ሰማይ ወምድር ክርስቶስ በሰው እጅ በተሠራ ቤት እንደማይኖር ይታወቅ ዘንድም ሰማያዊ ብሩህ ደመና ጋረደቻቸው፡፡ ‹‹በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት›› የሚል ቃል ከእግዚአብሔር አብ ዘንድ መጣ፡፡ ‹‹እርሱን ስሙት›› ማለቱም ጌታችን ዓለምን ለማዳን እንደሚሞት ሲናገር ቅዱስ ጴጥሮ ‹‹አይኹንብህ›› ብሎት ነበርና ‹‹እሞታለሁ›› ቢላችሁ ‹‹አትሞትም›› አትበሉት ሲል ነው፡፡ ሙሴና ኤልያስም ከጌታችን ጋር ሲነጋገሩ ተሰሙ፤ ስለ ክርስቶስ የተናገሩት ትንቢትም በደብረ ታቦር ተረጋገጠ፡፡ የፊቱን ግርማ ለማየትና የመለኮትን ድምፅ ለመስማት አልተቻላቸውምና ሙሴ ወደ መቃብሩ፣ ኤልያስም ወደ መጣበት ተመለሱ፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም የመለኮትን ፊት አይተው መቆም አልተቻላቸውምና ደንግጠው ወደቁ፡፡ ጌታችንም አጽናንቶ ኃይሉን ብርታቱን ካሳደረባቸው በኋላም እርሱ ከንቱ ውዳሴን የማይሻ አምላክ ነውና ዅሉም በጊዜው እስኪለጥ ድረስ ማለትም ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ተቀብለው የክርስቶስ አምላክነቱን፣ ሞቱን፣ ትንሣኤውን፣ ዕርገቱንና ዳግም ምጽአቱን ለዓለም እስኪሰብኩ ድረስ ያዩትም ምሥጢር ለማንም እንዳይነግሩ አዝዟቸዋል (ማቴ. ፲፯፥፩-፱፤ ማር.፱፥፪-፱)፡፡

በብሉይ ኪዳን ሊቀ ነቢያት ሙሴ ከእግዚአብሔር ጋር ሲነጋገር ቆይቶ ወደ ሕዝቡ ሲሔድ ፊቱ ያንጸባርቅ እንደ ነበርና የእስራኤላውያን ዓይን እንዳይጎዳ ሙሴ ፊቱን ይሸፍን እንደ ነበር ተጽፏል (ዘፀ. ፴፬፥፴፭)፡፡ ሙሴ የእግዚአብሔርን ድምፅ በመስማቱ ብቻ ፊቱ ያንጸባርቅ ከነበረ እግዚአብሔርን ፊት ለፊት በዓይን ተመልክቶ ብርሃኑን መቋቋምማ ምን ያህል ከባድ ይኾን?

እግዚአብሔር አምላክ በደብረ ታቦር ያደረገው መገለጥ በዘመነ ኦሪት ለሙሴ የሰጠውን ተስፋ ያስታውሰናል፡፡ ነቢዩ ሙሴ በዘመኑ ‹‹… አምላክነትህን (ባሕርይህን) ግለጽልኝ›› ሲል እግዚአብሔርን ተማጽኖት ነበር፡፡ እግዚአብሔርም ‹‹በባሕርዬ ፊቴን አይቶ የሚድን የለምና ፊቴን ማየት አይቻልህም እኔ በምገለጽልህ ቦታ ዋሻ አለና በብርሃን ሠረገላ ኾኜ እስካልፍ ድረስ በዋሻው ውስጥ ቁመህ ታየኛለህ፡፡ በባሕርዬ አይተህ ደንግጠህ እንዳትሞት በብርሃን ሠረገላ ኾኜ እስካልፍ ድረስ ቀዳዳ ባለው ዋሻ እሠውርሃለሁ፡፡ በብርሃን ሠረገላ ኾኜ ካለፍኹ በኋላ እጄን አንሥቼልህ ከወደ ኋላዬ ታየኛለህ እንጂ በባሕርዬ ግን ፊቴን ማየት አይቻልህም›› በማለት ለሙሴ ምላሽ ሰጥቶት ነበር፡፡ ይህም በፊት በፊት የሚጓዝ ሰው ኋላው (ጀርባው) እንጂ ፊቱ እንደማይታይ ጌታም በምልክት እንጂ በአምላክነቱ ለፍጡራኑ አለመገለጡን ያስረዳል፡፡ ምሥጢሩም አምስት ሺሕ ከአምስት መቶ ዓመት ሲፈጸም አምላክ ሰው ኾኖ ሥጋ ለብሶ በደብረ ታቦር በባሕርዩ እስኪገለጥለት ድረስ ሙሴ በመቃብር ተወስኖ እንደሚቆይ ያጠይቃል (ትርጓሜ ኦሪት ዘፀአት፣ ፴፫፥፲፫-፳፫)፡፡

እግዚአብሔር ‹‹ጀርባዬን ታያለህ›› ብሎ ለሙሴ በገባው ቃል መሠረት እነሆ በደብረ ታቦር በግርማ መለኮት፣ በክበበ ትስብእት (በለበሰው ሥጋ) ታየ፡፡ ነቢዩ ሙሴ ብርሃነ መለኮቱን በተመለከተ ጊዜም ‹‹ፊቴን ማየት አይቻልህም›› ያለው ቃሉ ይፈጸም ዘንድ የክርስቶስን ፊት ማየት አልተቻለውምና ወደ መቃብሩ ገባ፡፡ ኤልያስም ብርሃነ መለኮቱን አይቶ መቆም ስለ ተሳነው ወደ ብሔረ ሕያዋን ተመለሰ፡፡ የክርስቶስን መሞት በሥጋዊ ስሜት ተረድቶ ‹‹አይኹንብህ›› ያለው ቅዱስ ጴጥሮስ፤ መለኮታዊ ሥልጣንን የተመኙት ቅዱሳን ያዕቆብና ዮሐንስም አብሯቸው እየኖረ የማያውቁት ክርስቶስ የባሕርይ አምላክ መኾኑን በተረዱ ጊዜ ደንግጠው ወደቁ፡፡ እግዚአብሔር በደብረ ታቦር አንድነቱን፣ ሦስትነቱን ገለጠ፤ ከግርማ መለኮቱ የተነሣም ዓለም ተናወጠ፡፡

ጌታችን በዮርዳኖስ ሲጠመቅ የተገለጠው ምሥጢረ ሥላሴና የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት በደብረ ታቦር በገሃድ ተረጋግጧል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ የኾነው ደብረ ታቦር ምሥጢረ ሥላሴ ተገልጦበታል፤ የክርስቶስ አምላክነት ተመስክሮበታል፡፡ በደብረ ታቦር ብርሃነ መለኮቱ እንደ ተገለጠና የእግዚአብሔር አብ ምስክርነት እንደ ተሰማ ዅሉ ዛሬም በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ምሥጢረ ሥላሴ ሲነገር፣ የመለኮት ሥጋና ደም ሲታደል ይኖራል፡፡ በደብረ ታቦር ነቢያትም፣ ሐዋርያትም እንደ ተገኙ ዅሉ በቤተ ክርስቲያን ብሉይና ሐዲስ ኪዳን ይሰበካል፡፡ ሥርዓተ ቅዳሴ የሚፈጽሙ ልዑካን አምስት መኾናቸውም በደብረ ታቦር የተገኙትን ሙሴን፣ ኤልያስን፣ ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ዮሐንስን ያስታውሱናል፡፡ ዘወትር በቤተ መቅደሱ የሚፈተተው ኅብስትና የሚቀዳው ወይን ደግሞ በደብረ ታቦር የተገለጠው የጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋው፣ ክቡር ደሙ ነው፡፡

አንድም ደብረ ታቦር የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው፤ በደብረ ታቦር ነቢያትም ሐዋርያትም እንደ ተገኙ መንግሥተ ሰማያትንም ዅሉም ምእመናን በአንድነት ይወርሱታልና፡፡ ከመዓስባን ሙሴ፣ ከደናግል ኤልያስ መገኘታቸውም ደናግልም መዓስባንም በአንድነት ወደ መንግሥተ ሰማያትን እንደሚገቡ ያጠይቃል፡፡ አንድም ደብረ ታቦር የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክነቱንም ሰዉነቱንም በደብረ ታቦር እንደ ገለጠ ከእመቤታችን ከነፍስና ከሥጋዋ ጋር ተዋሕዶ ሰዉም አምላካም መኾኑን አሳይቷል፡፡ አምላክ ሰው፤ ሰውም አምላክ መኾኑ በድንግል ማርያም ማኅፀን ተገለጧል፡፡ በደብረ ታቦር ነቢያትም ሐዋርያትም እንደ ተገኙ እመቤታችንም የነቢያት ትንቢት ተፈጽሞባታል፤ የሐዋርያት ስብከት ጸንቶባታል፡፡ እርሷ አምላክን ለመሸከም ተመርጣለችና እመቤታችን በደብረ ታቦር ትመሰላለች፡፡ እንደዚሁም ደብረ ታቦር የአብያተ ጉባኤ (የአብነት ትምህርት ቤቶች) ምሳሌ ነው፡፡ በደብረ ታቦር የእግዚአብሔር ሦስትነት፣ አንድነት እንደ ታወቀ፤ ብርሃነ መለኮቱም እንደ ተገለጠ፤ ነቢያትና ሐዋርያትም እንደ ተገኙ ዅሉ በየአብነት ትምህርት ቤቶችም ምሥጢረ ሥላሴ፣ ነገረ መለኮት፣ ክብረ ቅዱሳን፣ ትንቢተ ነቢያትና ቃለ ወንጌል ዘወትር ይነገራል፣ ይሰበካል፤ ይተረጐማል፡፡

በአጠቃላይ ከጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዐበይት በዓላት መካከል አንደኛው የኾነው በዓለ ደብረ ታቦር እግዚአብሔር ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠበት በዓል በመኾኑ በቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ ነሐሴ ፲፫ ቀን በድምቀት ይከበራል፡፡ የአብነት ት/ቤት ደቀ መዛሙርትና ምእመናንም ብርሃነ መለኮቱን በደብረ ታቦር የገለጠ አምላክ ብርሃነ ምሥጢሩን በየልቡናቸው እንዲገልጥላቸው ለመማጸን ጸበል ጸሪቅ አዘጋጅተው ይዘክሩታል፡፡ ከዘመናት በፊት የተመኘውን የአምላኩን ፊት ከሙታን ተነሥቶ ለማየት የታደለው ሊቀ ነቢያት ሙሴ የተወለደውም በዚህች ዕለት ነው፡፡

እንዲህ እኛም በክርስቲያናዊ ምግባር ጐልምሰን፣ በትሩፋት ሥራ ከፍ ከፍ ብለን ከተገኘን በደብረ ታቦር እንደ ተደረገው ዅሉ በተቀደሰችው የእግዚአብሔር ተራራ በቤተ ክርስቲያን የሚፈጸሙ ምሥጢራትን ለመሳተፍ፣ የክርስቶስ ማደርያ በኾነችው በቅድስት ድንግል ማርያም እና ባለቤቱ ባከበራቸው በሌሎችም ቅዱሳን አማላጅነት ለመጠቀም፣ በየጉባኤ ቤቱ የሚቀርበዉን ጥበብ ለመቅሰም፣ በሚመጣው ዓለምም ሰማያዊ መንግሥቱን ለመውረስ እንበቃለን፡፡ አምላካችን በግርማ መለኮቱ ተገልጦ ለፍርድ በመጣ ጊዜ በቀኙ ያቆመን ዘንድም በክርስትና ሃይማኖት መጽናት፣ ትሕትናን ገንዘብ ማድረግ፣ በጥቅሉ በበጎ ምግባር መበርታት ይጠበቅብናል፡፡ ምሥጢረ መለኮቱን በደብረ ታቦር የገለጠ ጌታ ለእኛም መንፈሳዊውን አእምሮ፣ ማስተዋልና ጥበቡን ይግለጥልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በዓለ ደብረ ታቦር እና ቡሄ

ነሐሴ ፲፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጌታችን ምሥጢረ መለኮቱን ለገለጠበት ለበዓለ ደብረ ታቦር እንኳን በሰላም አደረሰን!

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ታቦር ብርሃነ መለኮቱን፣ ክብረ መንግሥቱን መግለጡን በማሰብ በየዓመቱ ነሐሴ ፲፫ ቀን በዓሉ በድምቀት ይከበራል፡፡ ይህ በዓል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ዘንድ ‹ቡሄ› በመባል ይታወቃል፡፡ ቡሄ ማለት ‹መላጣ፣ ገላጣ› ማለት ነው፡፡ በአገራችን ክረምቱ፣ ጭጋጉ፣ ደመናው ተወግዶ የብርሃን ወገግታ የሚታይበት በዚሁ በዓል አካባቢ ስለ ኾነ በዓሉ ‹ቡሄ› ተብሎ ይጠራል፡፡ በዓለ ደብረ ታቦር ጌታችን ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠበት፤ ብርሃን የታየበትና ድምፀ መለኮቱ የተሰማበ  ዕለት ስለ ኾነ ‹የብርሃን› ወይም ‹የቡሄ› በዓል ይባላል፡፡

ቡሄ ሲመጣ የክረምቱ ጨለማነት አልፎ ወደ ብርሃን፣ ወደ ጥቢ የሚያመራበት፤ ወደ መፀው የሚገባበት፤ ወገግታ የሚታይበት፤ ሰማይ ከጭጋጋማነት ወደ ብሩህነት የሚሸጋገርበት ወቅት በመኾኑ ከቡሄ በኋላ የጠነከረ ክረምት አይኖርም፡፡ ‹‹ቡሄ ከዋለ የለም ክረምት፤ ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት›› እንዲሉ፡፡ በአንዳንድ የአገራችን አካባቢዎች የቡሄ ዕለት ማታ ምእመናን ችቦ ያበራሉ፡፡ ይህም በደብረ ታቦር ለታየው ብርሃነ መለኮት ምሳሌ ነው፡፡ ሕፃናቱ ይህ በዓል ከመድረሱ በፊት ቀደም ብለው ጅራፍ ሲገምዱና ሲያጮኹ (ሲያኖጉ) ይሰነብታሉ፡፡ እናቶችም ለዚህ በዓል የሚኾን ዳቦ ለመጋገር ስንዴያቸውን ሲያጥቡ፣ ሲፈትጉ ይሰነብታሉ፡፡ በበዓሉ ዋዜማ (ነሐሴ ፲፪ ቀን) ሕፃናት በየቤቱ እየዞሩ ‹‹ቡሄ ና በሉ፤ ቡሄ በሉ፡፡ ቡሄ መጣ፤ ያ መላጣ፤ ቅቤ ቀቡት እንዳይነጣ …›› እያሉ ይጫወታሉ፡፡ በዚህ ጊዜ እናቶች ካዘጋጁት ዳቦ እያነሡ ይሰጧቸዋል፡፡ ሕፃናቱ ‹ቡሄ› የሚሉትም ዳቦውን ነው፡፡

ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን በገለጠበት ዕለት እረኞች ከብርሃኑ የተነሣ እየተገረሙና እየተደነቁ ወደ ቤት አልተመለሱም ነበር፡፡ የልጆቹን መዘግየት ያዩ ወላጆች ችቦ አብርተውና ዳቦ ይዘው ፍለጋ ወጥተዋል፡፡ ‹ቡሄ› ለሚሉ ልጆች ሙልሙል ዳቦ የሚሰጠውና በበዓሉ ችቦ የሚበራውም ከዚህ ታሪክ በመነሣት ነው፡፡ ለክርስትና ልጅ፣ ለአማች፣ ለምራት፣ ለዘመድ አዝማድ ዅሉ የቡሄ ዳቦ ይሰጣል፡፡ ልጆችም ዳቧቸውን እየገመጡ ጅራፍ ሲገርፉ ይውላሉ፡፡ የጅራፉ መጮኽ የድምፀ መለኮት ምሳሌ ሲኾን፣ ጅራፉ ሲጮኽ ማስደንገጡም ነቢያትና ሐዋርያት በድምፀ መለኮት መደንገጣቸውንና መውደቃቸውን ያስታውሳል፡፡

መምህረ ሐዋርያት ኢየሱስ ክርስቶስ ሦስቱን ተማሪዎቹን ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ዮሐንስን ይዞ በደብረ ታቦር ምሥጢር መግለጡን በማስታዎስ የአብነት ተማሪዎች ከመምህራቸው ጋር በመኾን በዓለ ደብረ ታቦርን (ቡሄን) ያከብራሉ፤ ስሙን ይጠራሉ፡፡ የአብነት ተማሪዎች ‹‹ስለ ደብረ ታቦር›› እያሉ እኽል ከምእመናን በመለመንና ገንዘብ በማዋጣት ጠላውን ጠምቀው፣ ዳቦውን ጋግረው፣ ቆሎውን ቆልተው ለደብረ ታቦር ዕለት ሊያስቀድሱ የመጡትን ምእመናን በመጋበዝና እርስበርስ በመገባበዝ፣ እንደዚሁም ቅኔ በማበርከት በዓለ ደብረ ታቦርን በታላቅ ድምቀት ያከብራሉ፡፡ ይህም እስከ አሁን ድረስ በአብነት ትምህርት ቤቶች የሚሠራበት ነባር ትውፊት ነው፡፡

ነገር ግን በአንድ አካባቢዎች በተለይ በከተማ ዙሪያ በዓለ ደብረ ታቦር (ቡሄ) ሃይማኖታዊ ትውፊቱን የለቀቀ ይመስላል፡፡ ለዚህም ልጆች የሚጫወቱበት መዝሙር ግጥሙና ዜማው ዓለማዊ መልእክት የሚበዛበት መኾኑ፤ በወቅቱ ችቦ ከማብራት ይልቅ ርችት መተኮሱና በየመጠጥ ቤቱ እየሰከሩ መጮኹ፤ ወዘተ. የበዓሉን መንፈሳዊ ትውፊት ከሚያደበዝዙ ተግባራት መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም በዚህ በዓል ገንዘብ ለመሰብሰብ ብቻ የሚሽቀዳደሙ ነገር ግን የበዓሉን ታሪካዊ አመጣጥ የማያዉቁ ልጆችም ጥቂቶች አይደሉም፡፡

ስለዚህ ወላጆች ለልጆቻቸው የበዓለ ደብረ ታቦርን መንፈሳዊነት፣ የመዝሙሮቹን ያሬዳዊነትና አከባበሩን ከቤተ ክርስቲያን መምህራን በመጠየቅ ማስተማር፤ ልጆችም ከወላጆች ወይም ከመምህራን በመጠየቅ የበዓሉን አከባበር መረዳትና የዚህን በዓል መንፈሳዊ ትውፊት ሳይበረዝ ለትውልድ ማስተላለፍ ይገባቸዋል፡፡ ‹‹ድምፅህን ሰማና በብሩህ ደመና፤ የቡሄው ብርሃን ለእኛ በራልን …›› የሚለውንና ይህን የሚመስሉ መንፈሳውያን መዝሙራትን እየዘመሩ በየቤቱ በመዘዋወር የሚያገኙትን ዳቦና ገንዘብ ለነዳያንና ለቤተ ክርስቲያን የሚሰጡ ልጆችንም ማበረታታትና አርአያነታቸውን መከተል ይኖርብናል፡፡

መልካም በዓል ይኹንልን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡-

መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ መ/ር አፈወርቅ ተክሌ፤ ፳፻፭ ዓ.ም፣ ገጽ ፫፻፲፭-፫፻፲፯፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ፤ ፳፻፯ ዓ.ም፣ ገጽ ፻፲፩፡፡

ደብረ ታቦር አምሳለ ቤተ ክርስቲያን – ካለፈው የቀጠለ

በመምህር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

ነሐሴ ፲፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

እንደዚሁም ተራራ ሲወጡት አድካሚ እንደ ኾነ መንግሥተ ሰማያትም በብዙ ድካም ትወረሳለች፡፡ ‹‹እስመ በብዙኅ ጻማ ሀለወነ ንባእ ውስተ መንግሥተ እግዚአብሔር፤ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በብዙ መከራ እንገባ ዘንድ አለን›› እንዲል (ሐዋ. ፲፬፥፳፫)፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃነ መለኮቱን በደብረ ታቦር የገለጸበት ምክንያት ምሥጢር በብዙ ድካም እንጂ ምንም ሳይደክሙ እንደማይገኝ ሲገልጽ ነው፡፡ ለደቀ መዛሙርቱ ብዙዎቹን ምሥጢራት የገለጠላቸው ከከተማ ውጭ ነው፡፡ ቀደም ሲልም ለሙሴ የቃል ኪዳኑን ጽላት ሲሰጠው ወደ ሲና ተራራ በመጥራት ነበር፡፡ ነገረ ሥጋዌዉንም በነበልባልና በእሳት አምሳል የገለጠለት በኮሬብ ተራራ በጎቹን አሰማርቶ በነበረበት ጊዜ እንደ ኾነ መጻሕፍት ይመሰክራሉ (ዘፀ. ፫፥፩)፡፡

ምሥጢር ይገለጥልን ባላችሁ ጊዜ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገስግሱ፤ ቤተ ክርስቲያንን ደጅ ጽኑ ለማለት ጌታችን ምሥጢሩን በተራራ ገለጠ፡፡ ወደ ተራራው ሲወጣም ስምንቱን ደቀ መዛሙርቱን ከይሁዳ ጋር ከተራራ እግር ሥር ትቶ ሦስቱን አስከትሎ ወጥቷል፡፡ ለሦስቱ በተራራው ላይ የተገለጠው ድንቅ ምሥጢርም ከእግረ ደብር ላሉት በሳምንቱ ተገልጧል፤ ከይሁዳ በቀር፡፡ ለዚህ ምሥጢር ብቁ ያልነበረው ይሁዳ ብቻ ነው፡፡ ይህም ተገቢውን ምሥጢር ለተገቢው ሰው መንገር እንደሚገባ፤ ለማይገባው ደግሞ ከመንገር መቆጠብ ተገቢ እንደ ኾነ ያስተምረናል፡፡ ‹‹እመኒ ክዱን ትምህርትነ ክዱን ውእቱ ለሕርቱማን ወለንፉቃን …፤ ወንጌላችን የተሰወረ ቢኾንም እንኳን የተሰወረባቸው ለሚጠፉት ነው፡፡ እግዚአብሔርን የሚመስለው የክርስቶስ የክብሩ ወንጌል ብርሃን እንዳያበራላቸው የዚህ ዓለም አምላክ ልባቸውን አሳውሯልና፤›› (፪ኛ ቆሮ. ፬፥፫-፭) በማለት ሐዋርያው የሰጠው ትምህርትም ይህን መሰል ምሥጢር ለሚገባው እንጂ ለማይገባው ሰው መግለጥ ተገቢ አለመኾኑን የሚያስረዳ ነው፡፡

፪ኛ የድል ተራራ ስለ ኾነ

ነቢዪቱ ዲቦራ የእስራኤል ጠላት የነበረው የኢያቢስን የሠራዊት አለቃ ሲሣራን ለመውጋት ወደ ደብረ ታቦር ዐሥር ሺሕ ሰዎችን አስከትሎ እንዲወጣ ለባርቅ ነግራዋለች (መሳ. ፬፥፮)፡፡ በዚህ መልኩ ባርቅ ዐሥር ሺሕ ሰዎችን አሰልፎ ዲቦራን አስከትሎ በደብረ ታቦር ሰፍሮ የነበረውን የሲሣራን ሠራዊት ድል ነሥቶበታል፡፡ ሲሣራ ዘጠኝ መቶ የብረት ሠረገላ እንደዚሁም ብዙ ሠራዊት በታቦር ያሰለፈ ቢኾንም ድል ግን ረድኤተ እግዚብሔርን ጥግ ላደረገው ለባርቅ ኾነ፡፡ በዚህ ጊዜ ዲቦራ በታቦር ተራራ የሙሴ እኅት ማርያም በኤርትራ ባሕር የዘመረችውን መዝሙር የመሰለ ምስጋና አቅርባለች፡፡ ዅሉም እስራኤላውያን የድል መዝሙር ዘምረውበታል፤ ፈጣሪአቸውን አመስግነውበታል፡፡ ጌታችንም የባሕርይ አምላክነቱን ገልጾ ከደቀ መዛሙርቱ ልቡና አጋንንትን የሚያባርርበት ዲያብሎስን ድል የሚነሳበት ስለኾነ ከሌሎች ተራሮች ተመርጧል፡፡

፫ኛ ትንቢት ስለ ተነገረለት

‹‹ታቦር ወአርሞንኤም በስመ ዚአከ ይትፌሥሑ ወይሴብሑ ለስምከ፤ ታቦርና አርሞንኤም በስምህ ደስ ይላቸዋል፤›› (መዝ. ፹፰፥፲፪) ብሎ ከክርስቶስ ሰው ኾኖ መገለጥ በፊት አምላካችን ክርስቶስ ብርሃነ መለኮቱን በደብረ ታቦር እንደሚገልጽ፣ ብርሃኑ ከደብረ ታቦር እስከ አርሞንኤም ድረስ እንደሚታይ፣ ይህም መለኮታዊ ብርሃን በታቦርና በአርሞንኤም ዙሪያ ለነበሩ ሕዝቦች ደስታ እንደሚኾን ቅዱስ ዳዊት ተናግሯል፡፡ ታቦር የተባለው ተራራ ከገሊላ ባሕር በምዕራብ በኩል በ፲ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኝ ሲኾን ተራራው እስከ ፭፻፸፪ ሜትር ከባሕር ጠለል (ወለል) ከፍ ይላል፡፡

ቀደም ሲል እንደገለጽነው ባርቅ ሲሣራን ድል ነስቶበታል፤ የመጀመሪያው የእስራኤል ንጉሥ ሳዖል በሳሙኤል እጅ ተቀብቶ ሲመለስ ‹‹ሦስት ሰዎች ታገኛለህ አንዱ ሦስት የድል ጠቦቶች፣ ሁለተኛው ሦስት ዳቦ ይዟል፤ ሦስተኛውም የወይን ጠጅ አቆማዳ ይዟል፡፡ ሰላምታ ይሰጡሃል›› ብሎ ሳሙኤል ነግሮት ነበር፡፡ በነገረው መሠረት ሦስት ሰዎችን አግኝቶበታል (፩ኛ ሳሙ. ፲፥፫-፭)፡፡ ስለዚህ ተራራ ቅዱስ ዳዊት በድጋሜ እንዲህ በማለት ትንቢት ተናግሮለታል፤ ‹‹የእግዚአብሔር ተራራ የለመለመ ተራራ ነው፡፡ የጸና ተራራ የለመለመ ተራራ ነው፡፡ እግዚአብሔር ይህን ተራራ ያድርበት ዘንድ ወደደው›› (መዝ. ፷፯፥፲፭) ብሎ እግዚብሔር ብርሃነ መለኮቱን እንደሚገልጥበት ዘምሮአል፡፡ በእነዚህ ከላይ በአየናቸው ሁለት ምክንያት ደብረ ታቦር ለዚህ ምሥጢር ተመርጧል፡፡

ጌታችን ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠው በምን ምክንያት ነው?

ነሐሴ ሰባት ቀን በቂሣርያ ደቀ መዛሙርቱን ‹‹ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል?›› ብሎ በጠየቃቸው ጊዜ ‹‹ኤርምያስ ነው፤ ኤልያስ ነው፤ ዮሐንስ መጥምቅ ነው፤ ከነቢያት አንዱ ነው ይሉሃል›› የሚል የተለያየ መልስ ሰጥተዉት ነበር፡፡ ‹‹እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ?›› ባላቸው ጊዜም ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ›› ብሎ መስክሯል፡፡ ስለዚህ ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን የገለጠው በሦስት ምክንያት ነው፤

፩ኛ በፍጡር ቃል የተመሰከረውን እውነት በባሕርይ አባቱ ለማስመስከር፤

፪ኛ ‹‹ከነቢያት አንዱ ነው›› ብለውት ነበርና እግዚአ ነቢያት (የነቢያት ጌታ) እንደ ኾነ ለማስረዳት፤

፫ኛ ክርስቶስ ‹‹እሰቀላለሁ፤ እሞታለሁ›› ባለ ጊዜ፣ ጴጥሮስ ‹‹ሐሰ ለከ፤ ልትሞት አይገባህም›› ብሎት ነበርና ‹‹እርሱን ስሙት›› የሚለዉን የእግዚአብሔር አብን መልእክት ለማሰማት፡፡

በፍጡሩ በጴጥሮስ የተመሰከረውን ምስክርነት የባሕርይ አባቱ ‹‹ይህ የምወደው ልጄ ነው፤ እርሱን ስሙት›› ማለት ‹‹‹እሞታለሁ፤ እሰቀላለሁ› ቢላችሁ ‹አይገባህም› አትበሉት፡፡ ዓለም የሚድነው በእርሱ ሞት ነውና ተቀበሉት›› ለማለት ነው፡፡ ‹‹ይህ ሊኾንብህ አይገባም›› ብሎት ነበርና ለጴጥሮስ መልስ እንዲኾን፡፡ ያዕቆብና ዮሐንስም ‹‹አንዳችን በቀኝህ አንዳችን በግራህ እንሾም›› ብለው ነበርና ፍቅረ ሲመትን ሊያርቅላቸውና የእርሱን የባሕርይ ክብሩን አይተው የመጣለት ዓላማ ልዩ መኾኑን እንዲረዱ ሲያደርጋቸው እነዚህን ሦስቱን ይዞ ወደ ተራራው ወጥቷል፡፡ ‹‹ከነቢያት አንዱ ነው›› ብለውት ነበርና ከነቢያት ሙሴንና ኤልያስን በተራራው ተገኝተው እንዲመሰክሩ አድርጓል፡፡ ሙሴ ‹‹የእኔ የሙሴን አምላክ ‹ሙሴ› የሚልህ ማነው? አምላከ ሙሴ፣ እግዚአ ሙሴ ይበሉህ እንጂ››፤ ኤልያስም ‹‹የእኔን አምላክ ‹ኤልያስ› የሚልህ ማነው? አምላከ ኤልያስ፣ እግዚአ ኤልያስ ይበሉህ እንጂ›› በማለት መስክረውለታል፡፡

ጌታችን ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠው እንዴት ነው?

ይህን ጥያቄ ለማብራራትም ኾነ ለመተንተን ዕውቀትም ቃላትም ያጥረናል፡፡ ወንጌላውያን መግለጥ በሚችሉት መጠን ከገለጹት ያለፈ ልናብራራው የምንችለው አይደለም፡፡ ማቴዎስ እንዲህ ይገልጸዋል፤ ‹‹ወተወለጠ ራዕዩ በቅድሜሆሙ ወአብርሀ ገጹ ከመ ፀሐይ ወአልባሲሁኒ ኮነ ፀዐዳ ከመ በረድ፤ በፊታቸውም ተለወጠ፡፡ ፊቱም እንደ ፀሐይ በራ፤ ልብሱም እንደ ብርሃን ነጭ ኾነ፤›› (ማቴ. ፲፯፥፪)፡፡ ወንጌላዊው በዚህ ዓይነት መንገድ የገለጸው ምሳሌ ስላጣለት ነው፡፡ ማርቆስም ይህንኑ ኃይለ ቃል ተጋርቶ ‹‹ልብሱም አንፀባረቀ፤ አጣቢም በምድር ላይ እንደዚያ ሊያነጣው እስከማይችል በጣም ነጭ ኾነ፤›› (ማር. ፱፥፪) በማለት ሲገልጸው፣ ሉቃስም በተመሳሳይ መልኩ ‹‹የፊቱ መልክ ተለወጠ፤ ልብሱም ተብለጭልጮ ነጭ ኾነ›› ሲል ገልጾታል (ሉቃ. ፱፥፳፱-፴)፡፡ እኛም ከዚህ ወንጌላውያን ከገለጹበት መንገድ የሚሻል ምሳሌ አናገኝለትም፡፡

ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን በደብረ ታቦር በገለጠ ጊዜ ፊቱን ማየት ተስኗቸው ነቢያት ወደየመጡበት መመለሳቸውን ሲያመላክቱ ኢትዮጵያዊቷ የቅኔ መምህርት እማሆይ ገላነሽ በቅኔአቸው እንዲህ በማለት አመሥጥረውታል፤

‹‹በታቦርሂ አመ ቀነፀ መለኮትከ ፈረስ

ኢክህሉ ስሒቦቶ ሙሴ ወኤልያስ››

ትርጕሙም፡- ‹‹መለኮት ፈረስህ በደብረ ታቦር በዘለለ ጊዜ ሙሴና ኤልያስ ሊስቡት አልቻሉም›› ማለት ሲኾን፣ ይህም ክርስቶስ በምን ዓይነት ግርማ እንደ ተገለጸ ያስረዳል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡