ደብረ ታቦር አምሳለ ቤተ ክርስቲያን – የመጀመርያ ክፍል

በመምህር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

ነሐሴ ፲፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹ወኮነት ደብረ ታቦር አምሳለ ቤተ ክርስቲያን እስመ አስተጋብአት እም ብሉይ ወሐዲስ፤ ደብረ ታቦር የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ነች፤ ከብሉይና ከሐዲስ ሰብስባለችና፡፡›› ምክንያቱም ከብሉይ ኪዳን ነቢያት ሙሴና ኤልያስን፤ ከሐዲስ ኪዳን ሐዋርያት ጴጥሮስን ያዕቆብን፣ ዮሐንስን ከመምህራቸው ከክርስቶስ ጋር ሰብስባለችና፡፡ ደግሞም ቤተ ክርስቲያን የተመሠረተችው በነቢያትና ሐዋርያት መሠረትነት ነውና፡፡ ‹‹እስመ ተሐነጽክሙ ዲበ መሠረተ ነቢያት ወሐዋርያት እንዘ ክርስቶስ ርዕሰ ማዕዘንተ ሕንጻ፤ በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል፤ የማዕዘኑም ራስ ደንጋይ ክርስቶስ ነው፤›› እንዲል (ኤፌ. ፪፥፳)፡፡

በዓለ ደብረ ታቦር

እንደሚታወቀው በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘጠኙ ዐበይት በዓላት አንዱ በዓለ ደብረ ታቦር ነው፡፡ በዓሉ ከዐበይት በዓላት የተመደበበት ምክንያትም በደብረ ታቦር የተገለጸው ምሥጢር ድንቅ በመኾኑ ነው፡፡ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ አንድ አንድ ጊዜ ለዅሉም፤ አንድ አንድ ጊዜ ደግሞ በከፊል ምሥጢራትን ገልጾላቸዋል፡፡ ከእነዚህ ምሥጢራትም የሚከተሉት ተጠቃሾች ናቸው፤ ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን በቤተ አልዓዛርና በቤተ ኢያኢሮስ፤ ምሥጢረ ቍርባንን እንደዚሁ በአልዓዛር ቤት፤ ነገረ ምጽአትን በደብረ ዘይት ገልጿል (ማቴ. ፱፥፳፫፤ ፳፮፥፳፮፤ ዮሐ. ፲፩፥፵፫)፡፡

ከእነዚህ ከላይ ከተዘረዘሩት ምሥጢራት መካከል ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንና ምሥጢረ ቊርባንን ዅሉም ደቀ መዛሙርት ያዩ ሲኾን ነገረ ምጽአትን ግን በከፊል ጴጥሮስ፣ ያዕቆብና ዮሐንስ አራተኛ እንድርያስን ጨምረው ተረድተዋል፡፡ የደብረ ታቦርን ምሥጢር ከዚህ ልዩ የሚያደርገው ከሐዋርያት ጴጥሮስ፣ ዮሐንስና ያዕቆብ ብቻ መገኘታቸው፤ ከነቢያት ደግሞ ሙሴና ኤልያስ መጨመራቸው ነው፡፡ ከጌታችን ዘጠኝ በዓላት አንዳንዶቹ በተፈጸመው ድርጊት የተሰየሙ ሲኾን ከፊሎቹ ድርጊቱ በተፈጸመባቸው ቦታዎች ተሰይመዋል፡፡ በድርጊቱ የተሰየሙት ፅንሰት፣ ልደት፣ ጥምቀት፣ ስቅለት፣ ትንሣኤ፣ ዕርገት ሲኾኑ ሁለቱ ሆሣዕና እና ጰራቅሊጦስ ደግሞ ድርጊትንና ስምን አስተባብረው የያዙ ናቸው፡፡ ከእነዚህ ዅሉ ተለይቶ ደብረ ታቦር ድርጊቱ በተፈጸመበት ቦታ ተሰይሟል፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከዅሉም ምሥጢራት ነገረ ምጽአቱንና ምሥጢረ መንግሥቱን በተራራ ላይ ገልጿል፡፡ ነገረ ምጽአትን በደብረ ዘይት የገለጸበትን ምክንያት ጠቢቡ ሰሎሞን ‹‹ለዅሉም ጊዜ አለው›› እንዳለው ለጊዜው ትተነው ወደ ደብረ ታቦር እንመለስ፤ ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን ለደቀ መዛሙርቱ የገለጠበት፤ ነቢያት ሊያዩት የተመኙትን ያዩበት ነቢያትና ሐዋርያት በአንድነት የተገናኙበት፤ ተገናኝተውም እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ኾነው የክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት የመሰከሩበት፤ እግዚአብሔር ወልድ በክበበ ትስብእትና በግርማ መለኮት የተገለጠበት፤ እግዚአብሔር አብ በደመና ‹‹የምወደው ለተዋሕዶ የመረጥኩት በእርሱ ህልው ኾኜ የምመለክበት ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት፤›› ብሎ የመሰከረበት፤ መንፈስ ቅዱስም በአምሳለ ርግብ የወረደበት፤ እግዚአብሔር አንድነቱን፣ ሦስትነቱን የገለጠበት እነ ቅዱስ ጴጥሮስ ለመኖር የተመኙት ደብረ ታቦር ነው፡፡ በዓሉ የጌታችን ሲኾን በስሙ ደብረ ታቦር ተብሏል፡፡ ይህ በዓል ያን ጊዜ ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን አስከትሎ ወደ ተራራው ሲወጣ፣ በተራራው ራስ ላይ ምሥጢሩን ሲገልጥላቸው፣ አእምሮአቸውን ሲከፍትላቸው፣ ከግርማው የተነሣ ፈርተው ሲወድቁና ሲያነሣቸው በዐይነ ሕሊናችን የምንመለከትበት በዓል ነው፡፡

ጌታችን ወደ ደብረ ታቦር የወጣው መቼ ነው?

ወንጌላዊያኑ ቅዱስ ማቴዎስና ቅዱስ ማርቆስ ጌታችን ምሥጢረ መለኮቱን ለመግለጥ ወደ ደብረ ታቦር የወጣው ደቀ መዛሙርቱን በቂሣርያ ‹‹ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል?›› ብሎ በጠየቃቸው በሰባተኛው ቀን እንደ ኾነ ጽፈዋል፡፡ ቅዱስ ሉቃስ ደግሞ በስምንተኛው ቀን ነው ይላል፡፡ (ማቴ. ፲፯፥፩-፰፤ ማር. ፱፥፪-፰፤ ሉቃ. ፱፥፳፰)፡፡ ነገሩ እንዴት ነው? ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ማቴዎስ በጠቀሰው በሰባተኛው ቀን መኾኑን በትርጓሜያቸው አስቀምጠዋል፡፡ ታዲያ ስለ ምን ስምንት አለ? የሚለውን ሲያትቱ (ሲያብራሩ) ስምንት ያለው ሰባት ሲል ነው ብለው ተርጕመውታል፡፡ ምክንያቱም አንድ ሳምንት የሚባለው ሰባት ቀን ነው፡፡

ሊቁ ቅዱስ አትናቴዎስ ስለ ዕለተ ሰንበት ሲናገር ‹‹ኦ ቅድስት ንዒ ኀቤነ ለለሰሙኑ ከመ ንትፈሣ ብኪ ለዓለመ ዓለምቅድስት ሆይ በየሳምንቱ ወደኛ ነዪ ለዘለዓለሙ በአንቺ ደስ ይለን ዘንድ፤›› በማለት መናገሩ ሰሙን ማለት ሳምንት እንደ ኾነ ያጠይቃል፡፡ ሳምንት ማለት ደግሞ ሰባት ቀን ነው፡፡ ከዚህ የተነሣ ሉቃስ በስምንተኛው ቀን ያለው በሳምንቱ (በሰባተኛው ቀን) ሲል ነው፡፡ በሌላ መልኩ ማቴዎስ በሰባተኛው ቀን ሲል ሉቃስ በስምንተኛው ቀን ማለቱ የወጡበትንና የተመለሱበትን ቈጥሮ ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ መጽሐፍ የጎደለውን ሞልቶ፣ የሞላውን አትርፎ መናገር ልማዱ ነው፡፡ ይህንም በሚከተሉት ኃይለ ቃላት መረዳት እንችላለን፤

  • ሰሎሞን ‹‹ወነበርኩ ውስተ ከርሠ እምየ ዐሠርተ አውራኃ ርጉዐ በደም፤ በእናቴ ማኅፀን በደም ረግቼ ዐሥር ወር ነበርኹ፤›› ብሏል (ጥበ. ፯፥፪)፡፡ የእናቶች እርግዝና ጊዜ ዘጠኝ ወር ኾኖ ሳለ ጠቢቡ ዐሥር ወር ተቀመጥሁ አለ፡፡ ይህን ያኽል ረጅም ቀን የመጨመር ልማድ ያለው መጽሐፍ ‹‹በስምንተኛው ቀን›› ቢል ብዙ የሚደንቅ፣ የሚጣረስም አይደለም፡፡ የሚጣረሰው ወይም የሚጋጨው የእኛ አእምሮ ነው፤ የዕውቀት ማነስ ስላለብን፡፡
  • ‹‹ወበጽሐ ወር ለኤልሳቤጥ፤ የኤልሳቤጥም የመውለጃዋ ወራት ደረሰ›› (ሉቃ. ፩፥፶፯) ሲል ቀን አልጠቀሰም፡፡ ሰው የሚወለድበት ቀኑ የታወቀ ስለ ኾነ ነው፡፡
  • ስለ እመቤታችን ሲናገር ‹‹በዚያ ሳሉም የመውለጃዋ ወራት ደረሰ የበኵር ልጅዋንም ወለደች›› ብሏል (ሉቃ. ፪፥፮)፡፡ ከአንድ በላይ የኾኑ ወሮች ‹‹ወራት›› ይባላሉ፡፡

ይህ ዅሉ የመጻሕፍት ቃል መጽሐፍ ሲያሻው ጠቅልሎ፣ ሲፈልግ ዘርዝሮ፣ አስፈላጊ ሲኾን ደግሞ በአኀዝ ወስኖ፣ ደግሞም አጕድሎ፣ እንደዚሁም ሞልቶ ሊናገር እንደሚችል ያስረዳናል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ በድንግል ማርያም ማኅፀን ያደረው ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ሲኾን መጽሐፍ ‹‹ተፀውረ በከርሣ ፱ተ አውራኃ፤ ዘጠኝ ወር በማኅፀኗ አደረ›› በማለት አምስት ቀን አጕድሎ ሲናገር እናገኘዋለን፡፡ ከዚህ አንጻር ሉቃስም አንድ ቀን ጨምሮ ተናግሯል፡፡ መጨመርም ማጕደል የመጻሕፍት ልማድ ነውና፡፡

ለዚህ ምሥጢር ደብረ ታቦር ለምን ተመረጠ?

፩ኛ ምሳሌነት ስላለው

የታቦር ተራራ፣ የቤተ ክርስቲያን፤ የወንጌል እና የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው፡፡ አንደኛውን ምሳሌ ከላይ የተመለከትን ሲኾን ሁለተኛው ምሳሌ አበው በትርጓሜአቸው እንዲህ አብራርተውታል፤ ተራራ ሲወጡት አድካሚ ነው፤ ከወጡት በኋላ ግን ዅሉንም ቁልጭ አድርጎ ሲያሳይ ደስ ያሰኛል፤ ወንጌልም ሲማሯት፤ ሲያስተምሯት ታደክማለች፤ ከተማሯት በኋላ ግን ጽድቅና ኀጢአትን፤ እውነትንና ሐሰትን ለይታ ስታሳውቅ ደስ ታሰኛለችና፡፡ በሌላ መልኩ ከተራራ ላይ ያለ ሰው ጠላቱን በቀላሉ በአፈር በጠጠር ድል መንሳት፣ ፍትወታት እኩያትን ማሸነፍ ይችላል፡፡ ከተራራ ላይ መሰወር እንደማይቻል በወንጌል ያመነ ሰውም ተሰውሮ አይቀርም፤ በመልካም ሥራው ለዅሉም ይገለጣል፡፡ በሦስተኛውም ተራራ የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው፡፡ ከነቢያት ሁለቱ ከሐዋርያት ሦስቱ በተራራው ላይ መገኘታቸው መንግሥተ ሰማያት ነቢያትም ሐዋርያትም በአንድነት የሚወርሷት መኾኗን ያስረዳል፡፡ ከደናግላን ኤልያስና ዮሐንስ፣ ከመዓስባን (በሕግ ጋብቻ ኖረው ሚስቶቻቸው የሞቱባቸው ወይም ትዳራቸውን የተዉ) ሙሴና ጴጥሮስ በተራራው ላይ መገኘታቸውም መንግሥተ ሰማያት ደናግላንም መዓስባንም መልካም ሥራ ሠርተው በአንድነት የሚወርሷት እንደ ኾነች ይገልጻል፡፡

ይቆየን

ማኅበረ ቅዱሳን መደበኛ የቴሌቭዥን መርሐ ግብሩን ሊቀጥል ነው

ነሐሴ ፲፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን መደበኛ የቴሌቭዥን መርሐ ግብሩን ከመስከረም ፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም ጀምሮ በልዩ ልዩ ቋንቋዎች ሊቀጥል ነው፡፡

በአሌፍ የቴሌቭዥን ጣቢያ በአዲስ ዓመት ልዩ ዝግጅት የሚጀምረው የማኅበሩ መንፈሳዊ የቴሌቭዥን መርሐ ግብር በአማርኛ፣ በአፋን ኦሮሞ እና በትግርኛ ቋንቋዎች የሚቀርብ ሲኾን፣ ሥርጭቱም ለጊዜው በየቀኑ ለሁለት ሰዓታት እንደሚተላለፍ የማኅበረ ቅዱሳን ጽ/ቤት አስታውቋል፡፡

ማኅበሩ ካሁን በፊት በኢቢኤስ የቴሌቭዥን ጣቢያ በሳምንት ለአንድ ሰዓት በአማርኛ ቋንቋ ሲያስተላልፍ የነበረው መንፈሳዊ መርሐ ግብር በልዩ ልዩ ምክንያት ከተቋረጠ በኋላ በየሳምንቱ ለሁለት ሰዓታት በኢንተርኔት ቴሌቭዥን በሚያሠራጫቸው መንፈሳዊ ዝግጅቶቹ ለሕዝበ ክርስቲያኑ ትምህርተ ወንጌል ሲያቀርብ ቆይቷል፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም የኦቢኤስ ቴሌቭዥን ጣቢያ ሥራ እስካቆመበት ጊዜ ድረስ በሳምንት ለሠላሳ ደቂቃ በአፋን ኦሮሞ ቃለ እግዚአብሔር ሲያስተምር መቆየቱ የሚታወስ ነው፡፡

በእግዚአብሔር መልካም ፈቃድ አገልግሎቱን ይበልጥ በማስፋት በመጪው አዲስ ዓመት በሚያስተላልፈው መንፈሳዊ የቴሌቭዥን ሥርጭቱም ኦርቶዶክሳዊውን አስተምህሮ ለሕዝበ ክርስቲያኑ ለማዳረስ ዝግጅቱን አጠናቋል፡፡

የቴሌቭዥን መርሐ ግብሩንም ከመስከረም ፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም ጀምሮ በሚከተለው የሥርጭት አድራሻ መከታተል የምትችሉ መኾኑን ማኅበሩ ያሳስባል፤

Aleph Television Nilesat (E8WB)

Frequency: 11595

Polarization: Vertical

Symbol Rate: 27500

FEC: 3/4

የተራራው ምሥጢር (ማቴ. ፲፯፥፩-፱)

በዲያቆን ታደለ ፈንታው

ነሐሴ ፲፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፊልጶስ ቂሣርያ ‹‹መነ ይብልዎ ሰብእ ለወልደ እጓለ እመሕያው፤ የሰው ልጅን ማን እንደ ኾነ ይሉታል?›› የሚል ጥያቄ ለደቀ መዛሙርቱ ባቀረበላቸው ጊዜ ‹‹አንዳንዱ መጥምቁ ዮሐንስ፣ ሌሎችም ኤልያስ፣ ሌሎችም ኤርምያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው ይላሉ›› የሚል ምላሽ አቀረቡ፡፡ ‹‹እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ?›› ብሎ በጠየቃቸው ጊዜም ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ «አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ» ብሎ ድንቅ የኾነ ምስክርነቱን ሰጠ (ማቴ. ፲፮፥፲፫-፲፬)፡፡ ጌታችን ‹‹የዮና ልጅ ስምዖን! እንደዚህ ዓይነቱን ምስክርነት ሥጋና ደም አልገለጸልህም፤ በሰማይ ያለው አባቴ እንጂ›› አለ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ በዚህ ምስክርነቱ ‹ብፁዕ› ተብሎ ተጠርቷል፡፡ በዘመናችን ብዙዎች የሥጋና ደም ዐሳብን ይዘው አምጻኤ ዓለማትነቱ፤ ከሃሊነቱ፤ ጌትነቱ፤ ተአምራቱ፤ መግቦቱ፤ ዓይን ነሥቶ ዓይን ለሌለው ዓይን መስጠቱ አልታያቸው ብሎ ‹አማላጅ› ይሉታል፡፡ ያለ ባሕርዩ ባሕርይ ሰጥተው በየመንደሩ፤ በየዳሱ አለ ብለው ይጠሩታል፤ እርሱ ግን ‹‹እነሆ ክርስቶስ በመንደር ወይም በእልፍኝ ውስጥ አለ ቢሏችሁ አትመኑ›› በማለት አስጠንቅቋል (ማቴ. ፳፬፥፳፫)፡፡ ከራሳቸው ልቡና አንቅተው ስለ ጌታችን የተሳሳተ መረዳት ያላቸው፣ ሰውንም የሚያሳስቱ የሥጋና ደም ዐሳባቸውን ቀላቅለው ንጹሑን የወንጌል ቃል የሚበርዙ ወገኖች ብፁዓን አልተባሉም፡፡

ይህ ምስክርነት በተሰጠ ማለትም ጌታችን በቂሣርያ ‹‹የሰውን ልጅ ማን ይሉታል?›› ብሎ በጠየቃቸው በሰባተኛው ቀን ከደቀ መዛሙርቱ ሦስቱን ይዞ ወደ ረጅምና ከፍ ወዳለ ተራራ ወጣ፡፡ ተራራውንም ሐዋርያት በሲኖዶስ ታቦር ብለው ጠቅሰውታል፡፡ በከፍታው ላይ ያለ ልዑል እግዚአብሔር ረጅምና ከፍ ያለ ነገርን ይወዳል፡፡ ንጉሡ ዖዝያን በሞተበት ዓመት ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ እግዚአብሔርን የተመለከተው በረጅምና ከፍ ባለ ዙፋን ላይ ነበር፡፡ ጌታችን ሰው ኾኖ ሥጋን ሲዋሐድም ከፍጥረታት ዅሉ ከፍ ያለውን አማናዊ ዙፋኑን የድንግል ማርያምን ማኅፀን ነበረ የመረጠው፡፡ ይኼንን ኹኔታ ሊቁ አባ ሕርያቆስ እንዲህ ብሎ በማድነቅ ይጠይቃል፤ ‹‹ድንግል ሆይ! ሰባት የእሳት መጋረጃ ከሆድሽ በስተየት በኩል ተጋረደ? በስተቀኝ ነውን? በስተግራ ነውን? ታናሽ ሙሽራ ስትኾኚ፡፡›› እግዚአብሔር ለአባታችን ያዕቆብ በራእይ የገለጸለት መሰላልም ከምድር ከፍ ያለ ነበረ፡፡ ምሳሌነቱም ከፍጥረታት ዅሉ ከፍ ላለች ለእመቤታችን ነው፡፡ ጌታችን ከፍ ያለ ነገርን መምረጡም ልዑለ ባሕርይ ነኝ ሲል ነው፡፡

በቅዱሱ ተራራ ላይ

ከሐዋርያት ሦስቱ ከነቢያት ሁለቱ በተገኙበት ልብሱ እሳት ክዳኑ እሳት የኾነ እግዚአብሔር ወልድ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፊታቸው ተለወጠ፡፡ አካሉ ሙሉ ብርሃን ሆነ፡፡ ጽጌያት ከአዕጹቃቸው እንዲፈነዱ ፊቱም እንደ ፀሐይ ብሩህ ኾነ፡፡ ልብሱም እንደ በረዶ ነጭ ኾነ፡፡ ክብሩን ግርማውን ጌትነቱን ገለጠ፡፡ ሙሴና ኤልያስ ከእርሱ ጋር ሲነጋገሩ ተሰሙ፡፡ ከደመናውም ውስጥ ‹‹ዝንቱ ውእቱ ወልድ ዘአፈቅር ዘቦቱ ሠመርኩ ወሎቱ ስምዕዎ፤ ልመለክበት የወደድኹት፣ ለተዋሕዶ የመረጥኹት ልጄ ይህ ነው፡፡ እርሱንም ስሙት›› የሚል አስፈሪ ድምፅ መጣ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹ከዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው›› አለ፡፡ አንተ የአምላክነት ሥራህን እየሠራህ ብንራብ እያበላኸን፣ ብንታመም እየፈወስከን፣ ብንሞት እያነሣኸን፤ ሙሴ የወትሮ ሥራውን እየሠራ – ደመና እየጋረደ፣ መና እያወረደ፣ ባሕር እየከፈለ፣ ጠላት እየገደለ፤ ኤልያስም እንደዚሁ ሰማይ እየለጎመ፣ እሳትን እያዘነመ፣ ዝናም እያቆመ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው፡፡ ሦስት አዳራሽ እንሥራ፤ አንዱን ለአንተ፤ አንዱን ለሙሴ፤ አንዱን ለኤልያስ አለ፡፡ ይህንን ገና እየተናገረ እንዳለ ብሩህ ደመና መጥቶ ጋረዳቸው፡፡ አብ የሰጠው ምስክርነትም ተሰማ፡፡ እመቤታችን በገሊላ ቃና ‹‹እርሱን ስሙት›› (ዮሐ. ፪፥፭)፡፡ በማለት ስለ ልጅዋ የሰጠቸው ምስክርነት ይኸው ነበረ፡፡ የተአምረ ማርያም ደራሲ ‹‹የእመቤታችን ዐሳብ እንደ እግዚአብሔር ዐሳብ ነው›› የሚለውም መንፈስ ቅዱስ የሚያናግረውን እንደዚህ ዓይነቱን ታላቅ ምስክርነት ነው፡፡

ጌታችን ግርማ መለኮቱን ስለ ምን ገለጠ?

ጸሐፍት ፈሪሳውያን የሕግ፣ ባለቤት ሠራዔ ሕግ እርሱ መኾኑን ባለመገንዘባቸው ሕግ ጥሷል በማለት በተደጋጋሚ ይከሱት ነበረ፡፡ አይሁድ ‹‹ይህ ሰው ከእግዚአብሔር አይደለም፤ ከእርሱስ ቢኾን ሰንበትን አይሽርም ነበር›› ብለዋልና ክርስቶስ ከእግዚአብሔር አብ እንደ ወጣ፣ የሰንበትም ጌታዋ እንደ ኾነ ይታወቅ ዘንድ ክብሩን መግለጥ ነበረበት፡፡ እንደ ገናም ‹‹ቃሌን የሚጠብቅ ቢኖር ለዘለዓለም ሞትን አይቀምስም›› በማለት ሲያስተምራቸው ‹‹በውኑ አንተ ከሞተው ከአባታችን ከአብርሃም ትበልጣለህን?›› ብለው ጠይቀውት እርሱም ‹‹እውነት እውነት እላችኋለሁ፤ አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ›› ብሏቸው ነበርና ክብሩን መግለጥ ነበረበት፡፡ በሕይወት ካሉት ኤልያስን፣ ከሞቱት ሙሴን የማምጣቱ ምሥጢር በሞትና በሕይወት ላይ ሥልጣን ያለኝ እኔ ነኝ ሲል ነው፡፡ ሙሴን ከመቃብር፣ ኤልያስን ከብሔረ ሕያውያን ማምጣቱም የሰማይና የምድር ገዢ እኔ ነኝ ሲል ነው፡፡ እንደ ገናም በሐዋርያቱ የተሰጠውን ምስክርነት በባሕርይ አባቱ በአብ ለማስመስከር ነው፡፡ አስቀድሞ ‹‹የሁለት ወገኖች ምስክርነት እውነት እንደ ኾነ ተጽፏል፡፡ ስለ እራሴ የምመሰክር እኔ ነኝ፤ አብ ስለ እኔ ይመሰክራል›› ብሎ ነበርና (ዮሐ. ፰፥፲፯)፡፡

በመጀመሪያ ተራራ የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው፡፡ ተራራን በብዙ ድካም እንዲወጡት መንግሥተ ሰማያትንም በብዙ መከራ ያገኟታልና፡፡ ይህንንም ቅዱስ ጳውሎስ ሲገልጥ ‹‹እስመ በብዙኅ ፃማ ሀለወነ ንባኣ ለመንግሥተ እግዚአብሔር፤ በብዙ ጭንቅ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እንገባ ዘንድ አለን›› በማለት አስረድቷል (ሐዋ. ፲፬፥፳፩-፳፪)፡፡ የደብረ ታቦሩን ምሥጢር ሲመሰክርም ቅዱስ ጴጥሮስ እንዲህ ሲል ይናገራል፤ ‹‹የእርሱን ግርማ አይተን እንጂ በብልሃት የተፈጠረውን ተረት ሳንከተል የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ኃይልና መምጣት አስታወቅናችሁ፡፡ ከገናናው ክብር ‹በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ እርሱ ነው እርሱን ስሙት› የሚል ያ ድምፅ በመጣለት ጊዜ ከእግዚአብሔር አብ ክብርንና ምስጋናን ተቀብሎአልና፡፡ እኛም በቅዱሱ ተራራ ከእርሱ ጋር ሳለን ይህ ድምፅ ከሰማይ ሲወርድ ሰማን፤›› (፩ኛ ጴጥ. ፩፥፲፮)፡፡

ለምን ደብረ ታቦርን መረጠ?

ጌታችን ምሥጢረ መለኮቱን በታቦር ያደረገው በሌላ ተራራ ያላደረገው አስቀድሞ ታቦር ትንቢት የተነገረበት ተራራ በመኾኑ ነው፡፡ ነቢዩ ዳዊት ‹‹ታቦር ወአርሞንኤም በስመ ዚአከ ይትፌሥሑ›› ብሎ ተናግሯል፡፡ ይህም በጌታችን ሰው መኾን የነቢያት ትንቢት ፍጻሜ ማግኘቱን የሚያሳይ ነው፡፡ ዐሥራ ሁለቱንም ደቀ መዛሙርት የመረጣቸው ጌታችን ነው፡፡ በመጀመሪያ ሙሴን ለመስፍንነት፣ አሮንን ለክህነት የመረጠበት ግብር እንዳልታወቀ ከደቀ መዛሙርቱ ሦስቱን የመረጠበትን ምክንያት የሚያውቀው እርሱ ብቻ ነው፡፡ እንደ ቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ግን ሦስቱን ወደ ተራራ ይዟቸው ስምንቱን ከእግረ ተራራው ጥሎአቸው የሔደው ምክንያት ስለ ነበራቸው ነው፡፡ የመጀመሪያው ከሌሎቹ የሚበልጡበት ምክንያት ነበራቸውና፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስን ይወደው ነበርና፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም ‹‹ጌታ ይወደው የነበረ ደቀ መዝሙር›› ተብሎ በብዙ ቦታ ተገልጧል፡፡ ቅዱስ ያዕቆብም ‹‹አንተ የምትጠጣውን ጽዋ እኛም እንጠጣለን›› ብሏል (ማቴ. ፳፥፳፪)፡፡ ዳግመኛም ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ›› ብሎ መስክሮ ስለ ነበረ ምስክርነቱ በእርሱ ብቻ የሚቀር ሳይኾን እግዚአብሔር አብም በደመና ኾኖ ‹‹በእርሱ ደስ የሚለኝ ልጀ እርሱ ነው እርሱን ስሙት›› በማለት የሰጠው ምስክርነት ከቅዱስ ጴጥሮስ ምላሽ ጋር ያለው ድንቅ ስምምነት ይገለጥ ዘንድ ነው፡፡ በዚህም ቅዱስ ጴጥሮስ የሰጠው ምስክርነት ሥጋና ደም ያልገለጠለት መኾኑ በተረዳ ነገር ታውቋል፡፡

ሙሴና ኤልያስ ለምን በተራራው ተገኙ

ሙሴና ኤልያስ በቅዱሱ ተራራ ከጌታችን ጋር የተነጋገሩ ነቢያት ነበሩ፡፡ በቅዱሱ ተራራ በተከበበ ብርሃን ውስጥ ኾነው ስማቸውን የጠቀስናቸውን ነቢያትን እንመለከታለን፡፡ እነዚህ ጾም የሚያስገኘውን ጥቅም ያሳዩ ናቸው፤ ዐርባ፣ ዐርባ ቀናትን ጾመዋልና፡፡ በቅዱሱም ተራራ ከተገኙት ቅዱሳን መካከል ናቸው፡፡ እነዚህ ለመገኘታቸው ምክንያት ነበራቸው፡፡ ጌታችን አስቀድሞ ‹‹እውነት እውነት እላችኋለሁ፤ ከዚህ ቁመው ካሉት የእግዚአብሔርን መንግሥት እስኪያዩ ድረስ የማይሞቱ አሉ›› ብሎ ተናግሮ ነበርና እግዚአብሔር ነቢዩ ኤልያስን እንዲገኝ አድርጓል፡፡ ሙሴ ደግሞ ‹‹እባክህ ፊትህን አሳየኝ›› ብሎ ለምኖት ነበር፡፡ እግዚአብሔርም ‹‹ፊቴን ማየት አይቻልህም፤ ነገር ግን ክብሬን በዓለቱ ላይ እተውልሃለሁ›› የሚል ተስፋ ለሙሴ ሰጥቶት ስለ ነበረ እግዚአብሔር የተናገረው ቃል ከሞት በኋላ እንኳን ተፈጻሚነቱ ይታወቅ ዘንድ ሙሴ በቅዱሱ ተራራ ላይ ተገኘ፡፡ ዳግመኛም ጌታችን ስለ ማንነቱ ሲጠይቃቸው ደቀ መዛሙርቱ ሰዎች ሙሴ፣ ኤልያስ፣ … እንደሚሉት ተናግረው ስለ ነበረ እርሱ አምላከ ሙሴና አምላከ ኤልያስ መኾኑ ይታወቅ ዘንድ ከነቢያት ሁለቱ ተገኙ፡፡ እንደገናም ሙሴ የሕጋውያን፤ ኤልያስ የደናግል ምሳሌ ነው፡፡ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የተጠሩት ሁለቱም ወገኖች ናቸውና ሁለቱ ነቢያት በደብረ ታቦር ተገኙ፡፡

ከደቀ መዛሙርት ሦስቱን ብቻ ለምን ይዞ ወጣ?

ያየዕቆብ እና የዮሐንስ እናት ማርያም ባውፍልያ ጌታችን መንግሥቱ ከዚህ ዓለም መስሎሏት ‹‹በነገሥህ ጊዜ እኒህ ልጆቼ አንዱ በቀኘህ አንዱ በግራህ እንዲቀመጡ አድርግልኝ?›› የሚል ልመናን ስለ ልጆችዋ አቅርባ ነበር፡፡ ጌታችንም መንግሥቱ ሰማያዊት እንጂ ምድራዊት አለመኾኗን ይገልጥላቸው ዘንድ ይዞአቸው ወደ ተራራ ወጣ፡፡ ስምንቱን ከእግረ ደብር ትቷቸው የወጣው በይሁዳ ምክንያት ነው፡፡ ክብሩንና መንግሥቱን እንዳያይ ይሁዳ ትንቢት ተነግሮበታልና ለይቶም እንዳይተወው ‹‹ከምሥጢረ መንግሥቱ ቢለየኝ ከሞቱ ገባሁበት›› ብሎ እንዳያስብ ምክንያት ለማሳጣት ስምንቱን ትቷቸው ወጣ፡፡

በዘመነ ኦሪት ከእስራኤል ሽማግሌዎች ሕዝቡን ያስተዳድሩ ዘንድ ሰባ ሰዎችን መርጦ ወደ ቅዱሱ ተራራ እንዲያቀርባቸው፤ ከመንፈሱ ወስዶ በሽማግሌዎቹ ላይ እንዲያፈስባቸውና ሙሴን እንዲያግዙት እግዚአብሔር ሙሴን አዝዞት ነበር፡፡ ሙሴም ከእያንዳንዱ ነገድ ስድስት ሰዎችን መረጠ፡፡ ከዐሥራ ሁለቱ ነገድ የተመረጡ ሰዎችም ሰባ ሁለት ኾኑ፡፡ ሙሴም እንደ ታዘዘው ሰባዎቹን ሰዎች ይዞ የቀሩትን ሁለቱን ኤልዳድንና ሞዳድን ከእግረ ደብር ትቷቸው ወደ ተራራው ወጥቷል፡፡ በደብረ ሲና ለሰባው ሊቃናት የተገለጠው ምሥጢር ከተራራው ሥር ለነበሩ ሁለቱ ሰዎችም ተገልጧል፡፡ በተመሳሳይ ኹኔታ በርእሰ ደብር (ደብረ ታቦር) ለሦስቱ ደቀ መዛሙርት የተገለጠው ምሥጢርም በእግረ ደብር ላሉ ለስምንቱም ተገልጦላቸዋል፡፡

ከዚህ ትምህርት የምንማረው ቁም ነገር

የቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ መሠረቱን በነቢያትና ሐዋርያት ላይ ያደረገ መኾኑን በቅዱሱ ተራራ ላይ የተገኙት ነቢያትና ሐዋርያት ምስክሮች ናቸው፡፡ እኛም ‹‹በነቢያትና ሐዋያርት መሠረት ላይ ታንጻችኋል›› ተብለናል፡፡ ስለ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማንነት የታመነ ምስክርነት አግኘተናል፡፡ አስቀድሞ ሐዋርያው ‹‹በመጀመሪያ ቃል ነበረ፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፡፡ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ፤›› (ዮሐ. ፩፥፩) በማለት የሰጠንን ምስክርነት፤ እንደ ገናም ‹‹ጸጋንና እውነትን ተመልቶ በእኛ ላይ አደረ›› በማለት የጠቀሰውን፤ ቅድመ ዓለም ከአብ ያለ እናት፣ በዚህ ዓለም ቅድስት ከምትኾን ከእመቤታችን ከድንግል ማርያም ያለ አባት የተወለደውን አምላክ ወልደ አምላክ በማመን የወንጌል ጋሻን ደፍተን፣ የእምነት ወንጌልን ተጫምተን በማመን እንበረታለን እንጂ ባለማመን ምክንያት አንጠፋም፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጠብቃ ካቆየቻቸው መንፈሳውያት እሴቶች መካከል በጌታችን፣ በእመቤታችንና በቅዱሳኑ ስም በዓላትን ማክበር ይገኙበታል፡፡ ከእነዚህም አንዱ የደብረ ታቦር በዓል ነው፡፡ በዓሉ ዳቦ በመድፋት፣ ጠላ በመጥመቅ በየቤቱ በደማቅ ሥርዓት ይከበራል፡፡ በተለይ የአብነት ተማሪዎች ከሕዝቡ በመለመን ስሙን ይጠራሉ፡፡ ይህም ልንጠብቀው የሚገባን መንፈሳዊ እሴታችን ነው፡፡ ጌታችን የቅዱሳኑን መታሰቢያ በተመለከተ ሲናገር ‹‹በደቀ መዝሙር ስም ቀዝቃዛ ውኃ ያጠጣ ዋጋው አይጠፋበትም›› በማለት ተናግሯል (ማቴ. ፲፥፵፪)፡፡ በቅዱሳኑ ስም የሚደረግ ምጽዋት ይህን ያህል በረከት ካስገኘ፣ በራሱ በባለቤቱ ስም የሚደረገውማ እንደምን አብዝቶ ዋጋ አያሰጥ? ክርስቲያኖች! በአጠቃላይ ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠበትን ከጌታችን ዐበይት በዓላት አንዱ የኾነውን የደብረ ታቦርን በዓል የምናከብረው በዚህ መንፈስ ነው፡፡ አምላካችን ‹‹ለሚወዱኝ እስከ ሺሕ ትውልድ ድረስ ምሕረትን የማደርግ እኔ እግዚአብሔር ነኝ›› (ዘፀ. ፳፩፥፮) ብሏልና በዓሉን በክርስቲያናዊ ሥርዓት በማክበር የበረከቱ ተሳታፊዎች መኾን ይገባናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የምሥጢር ቀን

በሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መልአክ፣

በምዕ/ጐጃም ሀገረ ስብከት የ፬ቱ ጉባኤያት መምህር

ነሐሴ ፲፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ከስምንተኛ መዓርግ ላይ ደርሶ የተፈጠረው የሰው ልጅ (አዳም) ሕገ እግዚአብሔርን ተላልፎ የተከለከለውን ዕፅ በመብላቱ የተሰጠው ጸጋ ስለ ተወሰደበት ምሥጢረ መለኮትን ማወቅ ተስኖት ነበር፡፡ የአምላክ ሰው መኾን አንዱ ምክንያትም ምሥጢረ መለኮት ለተሰወረበት ዓለም ምሥጢረ መለኮትን መግለጥ ነው፡፡ ጌታችን ወደዚህ ዓለም ሲመጣም ዓለም ምንም ምሥጢር አልነበራትም፡፡ ምሥጢራት ዅሉ በልበ መለኮት ተሰውረው ይኖሩ ነበር እንጂ፡፡ በሌላ አነጋገር የተፀነሰ እንጂ የተወለደ ምሥጢር አልነበረም፡፡ ለዚህም ነው መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  ለደቀ መዛሙርቱ ከሕዝብ ለይቶ ምሥጢራትን ይነግራቸው የነበረው (ማቴ. ፲፫፥፲፩)፡፡ በቀዳማዊው ሰው በአዳም በኩል ለሰው ልጀች ዅሉ የተሰጠው የመንግሥቱ ምሥጢር በሁለተኛው ሰው በክርስቶስ በኩል ዳግመኛ ተገለጠ፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ተናገረው ለቀደሙት ሰዎች በብዙ መንገድ በብዙ ኅብረ አምሳል ምሥጢራትን ይናገር የነበረ እግዚአብሔር ቅደመ ዓለም በነበረውና ተቀዳሚ ተከታይ በሌለው በአንድ ልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ተናገረ (ዕብ. ፩፥፩-፪)፡፡ ማንም ያየው የሌለ እግዚአብሔርነቱን ወደ ዓለም መጥቶ ተረከው፡፡ በአብ ልብነት ተሰውሮ ይኖር የነበረውን የመንግሥቱን ምሥጢርም ከልደቱ ጀምሮ በብዙ መንገድ ገልጦታል፡፡ በልደቱ ቀን ከገለጸልን ምሥጢር የተነሣ ‹‹ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት›› ብለን ዘመርን፡፡ ‹‹ይህንን ምሥጢር እናይ ዘንድ ኑ! እስከ ቤተልሔም እንሒድ›› (ሉቃ. ፪፥፲፭) ብለው ሲናገሩ ከእረኞች አፍ መስማታችንም ይህንኑ ምሥጢር ያስረዳል፡፡ ሶርያዊው ሊቅ ቅዱስ ኤፍሬም ይህን ሲያጸናልን ‹‹ንዑ ርዕዩ ዘንተ መንክረ፤ ይህን ድንቅ ምሥጢር ታዩ ዘንድ ኑ!›› በማለት ሕዝቡን በዓዋጅ ይጠራል፡፡

እግዚአብሔር ለሰው የገለጠው ምሥጢር ይህ ብቻ አይደለም፡፡ በፈጸመው የማዳን ሥራ በቤተ ኢያኢሮስ ምሥጢረ ድኅነትን፤ በቤተ አልዓዛር ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን፤ በጌቴሴማኒ ምሥጢረ ጸሎትን ካሳየ በኋላ በዕለተ ዐርብ መጋረጃው ተቀዶ የሰው ልጅ ባሕረ እሳትን ተራምዶ እስክናይ ድረስ ደገኛውን ምሥጢረ ድኅነት ገለጠልን፡፡ በደብረ ታቦር ደግሞ ምሥጢረ ሥላሴን ገልጦልናል፡፡ እግዚአብሔር ምሥጢራትን ለመግለጥ ሦስት መንገዶችን ይጠቀማል፤ እነዚህም ሰው፣ ጊዜ እና ቦታ ናቸው፡፡ በደብረ ዘይት የገለጠውን በደብረ ታቦር፣ በጌቴሴማኒ የገለጠውን በዮርዳኖስ፤ ለነቢያት የገለጠውን ለሐዋርያት አይገልጠውም፡፡ በተለይ በሐዋርያት ልቡና ያኖረውን፤ ከዅሉም በላይ ደግሞ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልቡና የሰወረውን ምሥጢሩን ማንም ፍጡር ሊያውቀው አይችልም፡፡ አበው እንደ ነገሩን በልበ ሐዋርያት ተሰውሮ የቀረውን የወንጌል ምሥጢር እስከ ዓለም ፍጻሜ የሚያውቀው የለም፡፡ ምክንያቱም የሐዋርያትን ክብር ካላገኙ ሐዋርያት ያወቁትን ማወቅ ስለማይቻል ነው፡፡ ከሐዋርያት በኋላ ተነሥቶ ወደ ሐዋርያት መዓርግ መድረስ የተቻለው ቅዱስ ጳውሎስ ብቻ ነው፡፡ ክብር ይግባውና መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ በደቀ መዛሙርቱ ልብ ሊያስቀምጠው የፈለገው አንድ ምሥጢር አለው፡፡ ይኸውም ጊዜው ሲደርስ የሚነገር፣ ከትንሣኤ በኋላ የሚበሠር እንጂ በማንኛውም ጊዜ የማይገለጥ አዲስ ምሥጢር ነው፡፡ ለዚህ ምሥጢር መገለጫ ይኾን ዘንድ የተመረጠው ቦታ ደግሞ ደብረ ታቦር ነው፡፡

ደብረ ታቦር ለምን ተመረጠ?

፩. ትንቢቱ፣ ምሳሌው ሊፈጸም 

በቀደመው ዘመን ነቢያት ትንቢት ከተናገሩላቸው ቅዱሳት መካናት አንዱ ደብረ ታቦር ነው፡፡ ነቢዩ ዳዊት በመዝሙሩ ‹‹ታቦር ወአርሞንኤም በስመ ዚአከ ይትፌሥሑ፤ ታቦርና አርሞንኤም በአንተ ስም ደስ ይላቸዋል›› (መዝ. ፻፹፰፥፲፪) በማለት ከደብረ ታቦር እስከ አርሞንኤም በደረሰው የመለኮት ብርሃን የተፈጠረውን ደስታ ሲገልጥ እንሰማዋለን፡፡ ምንድን ነው ይህ ደስታ? ሊባል ይችላል፡፡ ነቢዩ ከአንድ ሺሕ ዓመት በኋላ ስለሚደረገው፣ ተራሮችንና ኮረብቶችን ሳይቀር ስላስፈነደቀው ደስታ ይህን ትንቢት ተናገረ፡፡ ምናልባት ‹‹በአንተ ስም ደስ ይላቸዋል›› ብሎ ግዑዛን ለኾኑ ተራሮች ለሰው በሚናገር መልኩ መናገሩ ሊያስገርም ይችላል፡፡ የሰው የደስታው መገለጫ የገጹ ብሩህነት ነው፡፡ እነዚህ ተራሮችም በዚህ ዕለት በተገለጠው መለኮታዊ ነጸብራቅ የተነሣ ጨለማ ተወግዶላቸው የፀሐይን ብርሃን በሚበዘብዘው አምላካዊ ብርሃን፣ ብርሃን ኾነው የዋሉበት ቀን ነውና ነቢዩ ለሰው በሚናገርበት ግስ ተናግሮላቸዋል፡፡

ሌላም ምሥጢር አለው ይላሉ ሊቃውንቱ፤ ‹‹በአንተ ስም ደስ ይላቸዋል›› የሚለውን ኃይለ ቃል በተራሮች ስም የተጠሩት ልዑላኑ አገልጋዮች ነቢያትና ሐዋርያት በጌታ ስም ደስ ይላቸዋል ማለት ነው ብለው ይተረጕሙታል፡፡ ለምሳሌ በአባቶቻችን ዘመን በዚህ ቅዱስ ተራራ ጽኑ ሰልፍ እንደ ተደረገ በመጽሐፈ መሳፍንት እናነባለን (መሳ. ፬፥፩)፡፡ በእስራኤል ላይ ገዥ ኾኖ የተነሣው፣ በክፉ አገዛዙ ምክንያት እስራኤልን ያስለቀሰው አሕዛባዊው የሠራዊት አለቃ ሲሳራ ድል የተነሣው በዚሁ ሥፍራ ነበር፡፡ ደብረ ታቦር ዘጠኝ የብረት ሠረገሎች የነበሩትን ባለ ሠራዊት ሰው ሲሳራን ድል ለማድረግ ምቹ ቦታ ነበር፡፡ ያውም በጥቂት ኃይል በሴቲቱ ነቢዪት ዲቦራ በሚመራ የጦር ሠራዊት፡፡ ይህም በኋለኛው ዘመን ለሚደረገው የድል ዘመን ጥላ የኾነ ታሪክ ነው፡፡ አባቶቻችንን በብረት በትር ቀጥቅጦ የገዛውን ባለ ብዙ ሠራዊት ዲያብሎስን ከሴቲቱ ነቢዪት የተወለደው የይሁዳ አንበሳ ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ቅዱስ ሥፍራ ድል እንደሚያደርግላቸው፤ እስራኤል ዘነፍስንም ከዲያሎስ ባርነት ነጻ እንደሚያወጣቸው የሚያሳይ ምሥጢር ነበረው፡፡ ሲሳራን፤ ባራቅ እና ዲቦራ ድል ያደርጉታል ተብሎ ታስቦ ነበርን? ይልቁንም ሲገዛን ሊኖር አስቦ አልነበረምን? የድንግል ልጅ መድኃኒታችን ክርስቶስ ግን የሲኦልን በሮች ሰባብሮ ጠላታችንን በጽኑ ሥልጣን አስሮ ነጻ አወጣን፡፡ ምሳሌው አማናዊ የሚኾንበት ዘመን መድረሱን ሊያበስራቸውም ሐዋርያቱን መርጦ ወደ ደብረ ታቦር ይዟቸው ወጣ፡፡

፪. ደብረ ታቦር ዅሉን የሚያሳይ ቦታ ስለ ነበር

ደብረ ታቦር ላይ ቆሞ ዓለምን ቁልቁል መመልከት ይቻላል፡፡ ከተራራው ጫፍ ላይ ኾኖ  ሲመለከቱ ዅሉም በግልጥ ይታያል፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ዼጥሮስ  በዚህ ቦታ መኖርን የተመኘው ‹‹ሠናይ ለነ ሀልዎ ዝየ፤ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው›› (ማቴ. ፲፯፥፭) ሲል ነበር በተራራው የመኖር ፍላጎቱን የገለጠው፡፡ ደብረ ታቦር ዅሉንም ከላይ ኾኖ ለማየት የሚያስችል ከፍ ያለ ቦታ ነውና፡፡ ከዘመናት አስቀድሞ የተሰወረውን ምሥጢር ለዅሉ ግልጽ ሊያደርግ አስቦ ዅሉን ወደሚያሳየው ቦታ ወሰዳቸው፡፡ እግዚአብሔር ይህንን በምሥጢር አደረገ፡፡ በክርስቶስ ሰው መኾን ያልታየ ምሥጢር፣ ያልተገለጸ ድብቅ ነገር የለምና፡፡ አፈ በረከት ተብሎ የሚጠራው ቅዱስ ኤፍሬም በረቡዕ ውዳሴ ማርያም ላይ ‹‹የማይታወቅ ተገለጠ፤ የማይታይ ታየ›› ሲል የተናገረውም ስለለዚህ ነው፡፡ አሁን የማይታየውን እግዚአብሔርን የምናይባት ድብቁን የእግዚአብሔርን ነገር በእምነት የምናስተውልባት አማናዊቷ የታቦር ተራራ ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ በእርሷ ውስጥ የሚኖሩ ዅሉ ዓለምን ቁልቁል እየተመለከቱ ጣዕሟን ሲንቁባት ይኖራሉ፡፡ ከእርሷ ተለይተው ከላይ ከተራራው ጫፍ ኾነው ዓለምን ስለሚመለከቷት ቤታቸውን በተራራው ለማድረግ ይመኛሉ፡፡ ዅልጊዜም ‹‹እግዚአብሔርን አንዲት ልመና ለመንኹት፤ እሷንም እሻለሁ፤ በሕይወቴ ዘመን ዅሉ በእግዚአብሔር ቤት እኖር ዘንድ›› (መዝ. ፳፮፥፬) እያሉ ይዘምራሉ፡፡ ምክንያቱም በዚህ ዓለም ውስጥ ኾኖ የታቦር ተራራን (ቤተ ክርስቲያንን) ማየት አይቻልም፡፡ ከታቦር ተራራ (ቤተ ክርስቲያን) ላይ ኾኖ ግን የዓለምን ምሥጢር ማወቅ ይቻላልና፡፡

፫. በተራራ የተነጠቅነውን ጸጋ በተራራ ለመመለስ

አዳም እንደ አጥቢያ ኮከብ የሚያበራ፣ ግርማው የሚያስፈራ ብርሃናዊ ፍጡር እንደ ነበር፤ ሥነ ተፈጥሮውን የሚናገሩ መጻሕፍት ምስክሮቻችን ናቸው፡፡ ይህንን ብርሃናዊ የጸጋ ልብሱን ተጐናጽፎ የተቀመጠው በእግዚአብሔር ተራራ በገነት ነበር፡፡ ከመጀመሪያው ጀምሮ የጠላት ዐይን አርፎበት ኖሮ ከጥቂት ዓመታት በኋላ ይህን ብርሃናዊ ልብሱን ለብሶ እንደ ማለዳ ኮከብ እያበራ መኖር አልተቻለውም፡፡ እናም በዚያው በእግዚአብሔር ቅዱስ ተራራ ላይ ሳለ ይህን ጸጋዉን ባለማወቅ ተገፈፈ፡፡ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም የመጣው የተቀማነውን ጸጋ ለማስመለስ ነው፡፡ ስለዚህም በዚህ ቅዱስ ተራራ ላይ ለደቀ መዛሙርቱ በገለጠው ብርሃን ተስፋን አስጨበጠን፡፡ ቅዱስ ወንጌል እንደ ተናገረው በዚህ ዕለት ሐዋርያት፣ ነቢያት በተገኙበት በዚህ ሥፍራ የክርስቶስ አካል ብሩህ፤ ልብሱም ከበረዶ ይልቅ ነጭ ኾነ፡፡

የሰው ልጅ ከቅዱስ ተራራ ከገነት ከወጣበት ጊዜ ጀምሮ እንዲህ ኾኖ ታይቶ አያውቅም፡፡ ሰውነቱ በኃጢአት በልዞ በበደል መግነዝ ተገንዞ የሚያስቀይም መልክ ይዞ ይታይ ነበር እንጂ እንደዚህ ዓይነት መልክ አልነበረውም፡፡ ዛሬ ግን እንደዚያ አይደለም፤ የአዳም አካል መልኩ ተለውጧል፡፡ ከጥቁረቱ ነጽቷል፡፡ ወንጌላውያን ይህን ምሥጢር ሲገልጡት ‹‹ወተወለጠ ራዕዩ በቅድሜሆሙ፤ መልኩ በፊታቸዉ ተለወጠ›› (ማቴ. ፲፯፥፪፤ ማር. ፱፥፪)፡፡ ኢትዮጵያዊው ቄርሎስ ተብሎ የሚጠራው የአገራችን ሊቅ ቅዱስ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ይኼን ኃይለ ቃል ሲተረጕም ክርስቶስ በዚህ ዕለት የተገለጠው አዳም ከበደል በፊት በነበረው መልኩ እንደ ኾነ መጽሐፈ ምሥጢር በተሰኘው ድርሳኑ ይናገራል፡፡ ‹‹ዘይገሥሦሙ ለአድባር ወይጠይሱ፤ ተራሮችን በእጁ ሲዳስሳቸው የሚጤሱት›› ተብሎ ስለ እግዚአብሔር ኃያልነትና እርሱ ሲዳስሳቸው ተራሮች እንደሚቃጠሉ ሊጦን በተሰኘው የምስጋና ክፍል ተነግሯል፡፡ ታቦር ታዲያ እንደምን አልተናወጠችም? ሊቁ እንደ ተናገረው ባይኾን ኖሮማ ደብረ ታቦር ትፈራርስ ነበር፡፡

እግዚአብሔር ለሙሴ በተገለጠበት ተራራ ሕዝቡ የሚደርሱበትን አጥተው እስኪንቀጠቀጡ ድረስ ከባድ የመብረቅና የነጐድጓድ ድምፅ ይሰማ ነበር (ዘፀ. ፲፱፥፲፰)፡፡ አብርሃም ዮርዳኖስን ተሻግሮ የተገናኘውን የመልከ ጸዴቅን ግርማ በዐይኖቹ መመልከት አልችል ብሎ መልከ ጸዴቅ ቀርቦ እስኪያነሣው ድረስ በፊቱ እንደ በድን ኾኖ ወድቋል፡፡ የእስራኤል ልጆችም ከእግዚአብሔር ጋር ይነጋገር የነበረው የሙሴን ፊት ለማየት ተስኗቸው ፈርተዋል፡፡ የዛሬው ምሥጢር ግን ከዚያ ልዩ ነው፡፡ በደብረ ታቦር ከተገለጠው የእግዚአብሔር ክብር የተነሣ በዙሪያው የነበሩትን ዅሉ እንደ በድን ያደረገ የብርሃን ነጸብራቅ ከክርስቶስ ፊት ወጥቷል፡፡ ምሥጢሩም አዳም ከመርገም በፊት የነበረውን የጸጋ ግርማ ሞገስ የሚያሳይ ነው፡፡ ይኸውም በቅዱሱ የእግዚአብሔር ተራራ በገነት የተነጠቅነው ልጅነታች፤ እንደዚሁም የሚያስፈራና የሚያስደነግጥ ግርማ ሞገሳችን እንደ ተመለሰልን ያጠይቃል፡፡ በመጀመሪያው ሰው በአዳም ያጣነውን የልጅነት መልካችንን በሁለተኛው ሰው በክርስቶስ አገኘነው፡፡

እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ይህ ጸጋ በቤተ ክርስቲያን ሲታደል ይኖራል፡፡ ወንዶቹ በተወለዱ በዐርባ፤ ሴቶቹ ደግሞ በሰማንያ ቀናቸው ወደ ቤተ ክርስቲያን መጥተው በማየ ገቦ ተጠምቀው ዳግመኛ ከብርሃን ተወልደው ሰይጣንን የሚያስደነግጥ መልክ ይዘው ወደየቤታቸው ይመለሳሉ፡፡ ያስተውሉ! ደብረ ታቦር የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናት፡፡ በደብረ ታቦር ነቢያትና ሐዋርያት፣ መዓስባንና ደናግል፣ አረጋውያንና ወጣቶች እንደ ተገኙ ዅሉ ቤተ ክርስቲያንም በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ የታነጸች፤ ለመዓስባንና ለደናግል፣ ለአረጋውያንና ለወጣቶች ለመላው ሕዝበ ክርስቲያን የተዘጋጀች የእግዚአብሔር መገለጫ ተራራ ናት፡፡ ከነቢያት ሁለቱ፤ ከሐዋርያት ሦስቱ መገኘታቸው ዛሬ በቤተ መቅደስ የሚያገለግሉት አምስት ልዑካን ምሳሌ ነው፡፡ እነዚያ ክርስቶስን እንደ ታቦት በመኻል አድርገው እንደ ተገኙ፣ ዛሬም ልዑካኑ (አገልጋዮች) በቤተ ክርስቲያን በቃል ኪዳኑ ታቦት ዙሪያ የክብሩን ዙፋን ከበው ይቆማሉ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የፀረ ተሐድሶ አገልግሎት በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት

ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ፣ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፲፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹እንግዲህ ሒዱና በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው አሕዛብን ዅሉ አስተምሩ፤›› (ማቴ. ፳፰፥፲፱) በማለት ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ባዘዘው ቃል መሠረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረታዊ ተልእኮዋ ስብከተ ወንጌልን ለዓለም ማዳረስና ያላመኑትን በማሳመን፤ ያመኑትን እንዲጸኑ በማድረግ ዅሉንም ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ማቅረብ ነው፡፡ ነገር ግን አካላቸው ከውስጥ፣ ልቡናቸው ከውጭ የኾነ፤ ራሳቸውን ተሐድሶ ብለው የሚጠሩ፤ በኅቡዕም፣ በገሃድም አስተምህሮዋን የሚፃረሩና ምእመናኗን የሚያደናግሩ የቤተ ክርስቲያን ጠላቶች ለሐዋርያዊ ተልእኮዋ እንቅፋት ኾነውባታል፡፡ ይህን የመናፍቃንን ሤራ ለመከላከልም ልዩና ወጥ አሠራር መዘርጋት ተገቢ መኾኑ ስለ ታመነበት ቅዱስ ሲኖዶስ በወርኃ ግንቦት ፳፻፰ ዓ.ም ባደረገው ምልዓተ ጉባኤ የፀረ ተሐድሶ ዘኦርቶዶክስ ኮሚቴ እንዲቋቋም ውሳኔ አሳልፏል፡፡

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! በዛሬው ዝግጅታችን የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔ ከተግባር ላይ አውለው ሐዋርያዊ ተልእኳቸውን በትጋት እያከናወኑ ከሚገኙ አህጉረ ስብከት መካከል የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ፀረ ተሐድሶ ኮሚቴ አገልግሎትን በአጭሩ ልናስታውሳችሁ ወደድን፡፡ መልካም ንባብ!

መጋቤ ትፍሥሕት ሙሉጌታ ቸርነት፣ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ

በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ የሚመራው የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ዐሥራ አምስት ወረዳ አብያተ ክህነት እና ከአራት መቶ በላይ አብያተ ክርስቲያናት እንዳሉት ከጽ/ቤቱ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መጋቤ ትፍሥሕት ሙሉጌታ ቸርነት እንደ ገለጹልን፣ ሀገረ ስብከቱ ሰበካ ጉባኤያትን በየቦታው በማዋቀር፣ ሰባክያነ ወንጌልንና ካህናትን በመመደብ የስብከተ ወንጌል ተልእኮውን በማስፋፋት ላይ ይገኛል፡፡ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እንቅፋት የኾነውን የተሐድሶ ነን ባዮች መናፍቃንን እንቅስቃሴ ለመቈጣጠርም የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔ ተቀብሎ የፀረ ተሐድሶ ዘኦርቶዶክስ ኮሚቴን አቋቁሞ አገልግሎቱን ቀጥሏል፡፡ ከሥራ አስኪያጁ ማብራርያ እንደ ተረዳነው ኮሚቴው የተቋቋመው ከሀገረ ስብከት ጀምሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ነው፡፡ ዓላማው ምእመናን ከኑፋቄ ትምህርት ተጠብቀው በኦርቶዶክሳዊው አስተምህሮ ጸንተው እንዲኖሩ ማድረግ ሲኾን፣ አባላቱም ከሀገረ ስብከቱ ሠራኞች ጀምሮ ከካህናት፣ ከሰንበት ት/ቤት ወጣቶች፣ ከማኅበረ ቅዱሳን አባላትና ከምእመናን የተመረጡ ናቸው፡፡

‹‹የመናፍቃንን ሤራ ለማፍረስና ምእመናንን ከቅሰጣ ለመከላከል የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴው ድርሻ የጎላ ነው›› ይላሉ ሥራ አስኪያጁ የኮሚቴውን አስፈላጊነት ሲገልጹ፡፡ ሀገረ ስብከቱ በአፋጣኝ ኮሚቴ አቋቁሞ አገልግሎት መጀመሩ እንደሚያስመሰግነው የሚያብራሩት መጋቤ ትፍሥሕት ሙሉጌታ፣ በዚህ ተግባሩም ለሌሎች አህጉረ ስብከት እንደ አብነት ከመጠቀሱ አልፎ የልምድ ተሞክሮ በማካፈል ላይ መኾኑንም አስገንዝበዋል፡፡ በማኅበረ ቅዱሳን የአዳማ ማእከል ቤተ ክርስቲያን በሰጠችው አደራ መሠረት አባላቱን በማስተባበር፣ መመሪያ በማዘጋጀት፣ ሥልጠናዎችን በመስጠት፣ መረጃዎችን በማቅረብና የቁሳቁስ ድጋፍ በማድረግ ከሀገረ ስብከቱ ጎን ኾኖ የኮሚቴውን አገልግሎት እየደገፈ እንደሚገኝና የማእከሉ ድጋፍም ለሀገረ ስብከቱም ኾነ ለኮሚቴው ብዙ ሥራ እንዳቀለለት አስረድተዋል፡፡

ሊቀ ጉባኤ ቆሞስ አባ ተክለ ሃይማኖት ወልዱ፣ በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት የናዝሬት ደብረ ፀሐይ ቅድስት ማርያም ካቴድራል አስተዳዳሪ እና የሀገረ ስብከቱ ፀረ ተሐድሶ ዘኦርቶዶክስ ኮሚቴ ሰብሳቢ

በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት የናዝሬት ደብረ ፀሐይ ቅድስት ማርያም ካቴድራል አስተዳዳሪ ሊቀ ጉባኤ ቆሞስ አባ ተክለ ሃይማኖት ወልዱ ደግሞ የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴው ሰብሳቢ ናቸው፡፡ እርሳቸው እንዳብራሩት ኮሚቴው አገልግሎቱን የጀመረው በወርኃ ታኅሣሥ ፳፻፱ ዓ.ም ሲኾን፣ ወደ አገልግሎት ከመግባቱ አስቀድሞ መተዳደርያ ሕጉንና የሥነ ምግባር ደንቡን፣ እንደዚሁም የሥልጠና ሰነዱን በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ከማጸደቁ ባሻገር ለአባላቱ የሥራ ድርሻቸውን አሳውቋል፡፡ የኮሚቴውን ዓላማ ለምእመናን ማስተዋወቅ፤ በየዐውደ ምሕረቱ የሚሰጠው ትምህርት ተጠናክሮ እንዲቀጥል ማድረግና ሥልጠና መስጠት ከኮሚቴው ተግባራት መካከል የሚጠቀሱ ሲኾን፣ የመናፍቃንን እንቅስቃሴ፣ ጫናዎቹንና መከላከያ መንገዶቹን በማመላከት ኦርቶዶክሳዊውን አስተምህሮ ማሳወቅም በሥልጠናው የተካተቱ ጉዳዮች ናቸው፡፡ ኮሚቴው፣ ካሁን ቀደም ለሀገረ ስብከቱና ለየወረዳ ቤተ ክህነቱ ሠራተኞች፣ ለካህናት፣ ለሰንበት ት/ቤት አባላትና ለማኅበረ ምእመናን የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርትና ሥልጠና ሰጥቷል፡፡ ሥልጠናውም በናዝሬት ከተማ በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ሙሉ ለሙሉ የተሰጠ ሲኾን፣ በየገጠሩ ለሚኖሩ ምእመናንም በቅርብ ጊዜ እንዲዳረስ ይደረጋል፡፡

ከሰብሳቢው ገለጻ እንደ ተረዳነው ስለ መናፍቃን እንቅስቃሴ መረጃ በማሰባሰብና ለምእመናን የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና በመስጠት አገልግሎቱን የጀመረው ኮሚቴው፣ ወደፊትም ይህን መንፈሳዊ ተልእኮዉን አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡ ተግባሩን በሥርዓት ለማከናወን እንዲያመቸውም በሳምንት አንድ ቀን ጉባኤ ያካሒዳል፡፡ የኮሚቴው አባላት እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ኾነው መሥራታቸው፤ ምሥጢር ጠባቂነታቸው፤ ከራስ ሐሳብና ጥቅም ይልቅ የቤተ ክርስቲያንን ጉዳይ የሚያስቀድሙና ልዩነቶችን በውይይት የመፍታት ልምድ ያዳበሩ መኾናቸው ለአገልግሎቱ መፋጠን ከፍተኛ አስተዋፅዖ አለው ይላሉ ሊቀ ጉባኤ የአባላቱን ጥንካሬ በማድነቅ፡፡

ማኅበረ ምእመናን ኦርቶዶክሳዊውን አስተምህሮ በሚገባ እንዲያውቁ የሚያበቃ ትምህርትና ሥልጠና መስጠት፤ በየዐውደ ምሕረቱ የሚቀርበው ትምህርተ ወንጌል በስፋት እንዲቀጥል መደገፍ፤ የአፅራረ ቤተ ክርስቲያን እንቅስቃሴ እንዲዳከምና ኦርቶዶክሳዊው አስተምህሮ እንዲስፋፋ ማድረግ፤ ሐሰተኞች መምህራንን በመከታተል ከስሕተታቸው እንዲታረሙ መምከር፤ ካልተመለሱም ተወግዘው እንዲለዩ ለቅዱስ ሲኖዶስ ማቅረብ ኮሚቴው ወደፊት ለማከናወን ያቀዳቸው ተግባራት መኾናቸውንም ሊቀ ጉባኤ ቆሞስ አባ ተክለ ሃይማኖት ጨምረው ገልጸዋል፡፡ አያይዘውም አፅራረ ቤተ ክርስቲያን በተለይ ራሳቸውን ‹ተሐድሶ› ብለው የሚጠሩ መናፍቃን ማን ይነካናል ብለው በድፍረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እየተሳደቡ፣ አባቶችንም እያጥላሉ እንደ ኾነ፤ የተሳሳተ ትምህርታቸውን ለማስፋፋት ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ እንደሚገኙ፤ ቍጥራቸውም በዘመናት ሳይኾን በቀናት እየጨመረ እንደ መጣ ጠቅሰው፣ በሀገረ ስብከቱ የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴ የተቋቋመው እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ ይህን የመናፍቃኑን እንቅስቃሴ ለመከላከል መኾኑን አብራርተዋል፡፡

አቶ ኃይለ ኢየሱስ ከበረ፣ የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴው ጸሐፊ

የፀረ ተሐድሶ ዘኦርቶዶክስ ኮሚቴው ጸሐፊ አቶ ኃይለ ኢየሱስ ከበረ በበኩላቸው ኮሚቴው ከሀገረ ስብከቱ ጀምሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ባለው መዋቅር ልዩ ልዩ ክፍሎችን የሚመሩ ሰባት አባላት እንዳሉት፤ ከክፍሎቹ መካከልም የትምህርትና ግብረ መልስ፣ መረጃና ትንተና፣ ቁጥጥርና ክትትል፣ እንደዚሁም የመርሐ ግብር ክፍል ተጠቃሾች መኾናቸውን አስታውሰው፣ የመናፍቃንን እንቅስቀሴ በሚመለከት ለወጣቶች ልዩ ሥልጠና ለመስጠት መታቀዱንም ጠቁመዋል፡፡ ጸሐፊው እንዳስረዱት፣ ኮሚቴው ለመጀመሪያ ጊዜ እንደ መቋቋሙ የልምድ ማነስ፣ የመረጃ ችግር፣ የድጋፍ ሰጪ አካላት እጥረት እና የመናፍቃን እንቅስቃሴ በፍጥነት መስፋፋት ከመሰናክሎች መካከል የሚጠቀሱ ሲኾን፣ በአዎንታዊ መልኩ ከሀገረ ስብከት እስከ አጥቢያ የሚደርስ ሰፊ መዋቅር ያለው መኾኑ፤ አገልግሎቱ በአጭር ጊዜ ውስጥ በስፋት መዳረሱ፤ ወጥነት ባለው አሠራር መዋቀሩ የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴውን አገልግሎት በአርአያነት እንዲጠቀስ ያደርገዋል፡፡

በመጨረሻም የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ፣ የኮሚቴው ሰብሳቢ እና ጸሐፊው የሚከተለውን መልእክት አስተላልፈዋል፤

‹‹በቤተ ክርስቲያን ላይ ፈተና ቢበዛባትም የተመሠረተችው በክርስቶስ ደም ነውና አትሸነፍም›› የሚሉት መጋቤ ትፍሥሕት ሙሉጌታ ቸርነት፣ የኮሚቴው ዓላማ ከግብ ደርሶ የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ ተልእኮ ለማፋጠን ይቻል ዘንድ አባቶች ምእመናንን ተግተው ቃለ እግዚአብሔርን እንዲያስተምሩ፤ ምእመናኑም ትክክለኛ እረኞቻቸውን በመለየት ቃሉን እንዲማሩ፤ በአጠቃላይ መላው ሕዝበ ክርስቲያን በፈተናዎች ሳይደናገጡ በጸሎት እንዲበረቱና ራሳቸውንም ሌሎችንም ከኑፋቄ ትምህርት በመጠበቅ ክርስቲያናዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡

ሊቀ ጉባኤ ቆሞስ አባ ተክለ ሃይማኖት ወልዱ በበኩላቸው፤‹‹ከአሁን በፊት የተሐድሶ መናፍቃን ጉዳይ የማኅበረ ቅዱሳን የፈጠራ ወሬ ነው ይባል ነበር፡፡ አሁን ግን ጉዳዩ ቤተ ክርስቲያንን የሚፈታተን መኾኑ ተደርሶበታል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም የመናፍቃኑን እንቅስቃሴ በመከላከል ረገድ ከሕዝበ ክርስቲያኑ ጋር ኾኖ የሚጠበቅበትን የልጅነት ድርሻ በመወጣት ላይ ነው፡፡ ወደፊትም በዚህ መንፈሳዊ አገልግሎቱ ሊቀጥል ይገባል›› ሲሉ አባታዊ ምክራቸውን ለግሰዋል፡፡ በተጨማሪም የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴው ዓላማ ኦርቶዶክሳዊውን አስተምህሮ በማስጠበቅ እነርሱን ለመንግሥተ ሰማያት ማዘጋጀት እንደ ኾነ ተገንዝበው፣ በመላው ዓለም የሚገኙ ምእመናን በሐሳብ፣ በገንዘብ፣ በዕውቀት፣ ወዘተ. በመሳሰሉ መንገዶች አገልግሎቱን በመደገፍ የቤተ ክርስቲያንን ችግር ሊቀርፉና የስብከተ ወንጌል ተልእኮውን ሊያስፋፉ እንደሚገባ በኮሚቴው ስም ጥሪ አቅርበዋል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ፣ የሀገረ ስብከቱ፣ የየወረዳ አብያተ ክህነቱና የየሰበካ ጉባኤያቱ ሠራተኞች፤ የየሰንበት ት/ቤቶች ወጣቶች፣ የማኅበረ ቅዱሳንና የሌሎችም መንሳውያን ማኅበራት ድጋፍ ኮሚቴው አገልግሎቱን በአግባቡ እንዲወጣ አድርጎታል የሚሉት አቶ ኃይለ ኢየሱስ ከበረ ደግሞ፣ ለወደፊትም ከዚህ በበለጠ ውጤታማ ይኾን ዘንድ የአባቶች፣ የወንድሞችና እኅቶች ተሳትፎ እንዳይለየን ሲሉ ድጋፍ ጠይቀዋል፡፡ የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴውን ዓላማ በፍጥነት ከግብ ለማድረስ ይቻል ዘንድም ዅሉም ምእመናን በተለይ የሰንበት ት/ቤትና የማኅበረ ቅዱሳን አባላት የመናፍቃንን እንቅስቃሴ እየተከታተሉ ለኮሚቴው እንዲያቀርቡ፤ ማኅበረ ቅዱሳንን የመሰሉ ድጋፍ ሰጪ አካላትም በቁሳቁስ፣ በገንዘብ፣ በሐሳብ፣ በመረጃ አቅርቦትና ሥልጠና በመስጠት ድጋፋቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ በማሳሰብ ጸሐፊው መልእክታቸውን አጠቃለዋል፡፡

ዝግጅት ክፍላችንም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት አስተምህሮ ሳይበረዝና ሳይከለስ ለትውልዱ ይዳረስ ዘንድ የፀረ ተሐድሶ ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ኮሚቴ እንዲቋቋም ውሳኔ በማሳለፉ ለቅዱስ ሲኖዶስ ያለውን አክብሮት እየገለጸ፣ እንደ ምሥራቅ ሸዋ ዅሉ ሌሎች አህጉረ ስብከትም ሐዋርያዊ ተልእኮውን እንዲያስፋፉና የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴ አቋቋመው የመናፍቃንን ሤራ እንዲከላከሉ በመደገፍ ዅላችንም የቤተ ክርስቲያናችንን አስተምህሮ የመጠበቅና የማስጠበቅ ሓላፊነታችንን እንወጣ ሲል ያሳስባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የወደቁትን እናንሣ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹እናንተ የአባቴ ቡሩካን፣ ዓለም ሳይፈጠር የተዘጋጀላችሁን መንግሥት ትወርሱ ዘንድ ኑ፡፡ ተርቤ አብልታችሁኛልና፤ ተጠምቼ አጠጥታችሁኛልና፤ እንግዳም ኾኜ ተቀብላችሁልና፡፡ ታርዤ አልብሳችሁኛልና፤ ታምሜም ጐብኝታችሁኛልና፤ ታስሬም ወደ እኔ መጥታችሁ ጠይቃችሁኛልና፤›› (ማቴ. ፳፭፥፴፬-፴፯) ተብሎ በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈው፣ ክርስቲያኖች የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ ከምንበቃባቸው ትእዛዛት መካከል አንደኛው ሰዎችን መርዳት ነው፡፡ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰዎችን መርዳት የሚያስገኘውን ሰማያዊ ዋጋ ሲገልጽም ‹‹በእኔ ካመኑ ከእነዚህ ከታናናሾች ወንድሞቼ ለአንዱ ያደረጋችሁትን ዅሉ ለእኔ አደረጋችሁት፤›› በማለት ቃል ኪዳን ሰጥቷል (ማቴ. ፳፭፥፵)፡፡

ይህን ቃል ባለማስተዋልና በሥጋዊ ስንፍና በመያዝ ለራሳችን ድሎት ብቻ የምንሽቀዳደም ራስ ወዳዶች ብዙዎች ብንኾንም፣ በአንጻሩ ቃሉን ተስፋ በማድረግ በገዛ ፈቃዳቸው ተነሣሥተው፣ በማኅበር ተሰባስበው ሰዎችን በመርዳት ክርስቲያናዊ ተግባር የሚፈጽሙ በጎ አድራጊ ምእመናን በየአገሩ አሉ፡፡ ጧሪ ቀባሪ ያጡ ሕሙማንንና አረጋውያንን የማሳከም፣ የመከባከብና ራሳቸውን እንዲችሉ የማገዝ ዓላማና ርእይ ሰንቀው በአዲስ አበባ ከተማ ከተቋቋሙ የበጎ አድራጎት ማኅበራት መካከል የወደቁትን አንሡ የነዳያን መርጃ ማኅበር አንዱ ነው፡፡ የማኅበሩ ተቋማዊ ጠባይዕና አሠራር ምን ዓይነት ነው? የገቢ ምንጩ ምንድን ነው? ሒሳብ አያያዙስ እንዴት ነው? ድጋፍ የሚያስፈልጋቸውን ሰዎች የሚያሰባስበው በምን ዓይነት መሥፈርት ነው? የሚሉና ሌሎች ጥያቄዎችን አንሥተንላቸው፣ የማኅበሩ መሥራች አቶ ስንታየሁ አበጀ ማብራርያ ሰጥተውናል፡፡ የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! በዛሬው ዝግጅታችን፣ መሥራቹ የሰጡንን ቃለ ምልልስ እና ማኅበሩ ባሳተመው ብሮሸር ላይ የተጠቀሱ ተግባራቱን መነሻ በማድረግ የማኅበሩን አገልግሎት እናስቃኛችኋለን፡፡ መልካም ንባብ!

አቶ ስንታየሁ አበጀ፣ የማኅበሩ መሥራች

የወደቁትን አንሡ የነዳያን መርጃ ማኅበር ከዐሥራ ዘጠኝ ዓመታት በፊት በአቶ ስንታየሁ አበጀ አስተባባሪነት ተመሠረተ፡፡ እኒህ ምእመን በደረሰባቸው ሥጋዊ ችግር ምክንያት ጠያቂ አጥተው በየጎዳናውና በየመቃብር ቤቱ ሲንገላቱ ኖረው ከዓመታት በኋላ ቆመው መሔድ ስለ ተቻላቸው ‹‹እግዚአብሔር በልዩ ጥበቡ እኔን ከወደቅሁበት ያነሣኝ ለትምህርት ነው፡፡ ስለዚህ እንደኔ የሚጠይቃቸው ያጡ ሰዎችን ከየወደቁበት ማንሣት አለብኝ›› የሚል መልካም ርእይ ሰንቀው፣ ከበጎ ፈቃደኞች ጋር ኾነው መስከረም ፩ ቀን ፲፱፻፺ ዓ.ም ‹‹የወደቁትን አንሡ›› በሚል ስያሜ የነዳያን መርጃ ማኅበር አቋቋሙ፡፡ ማኅበሩ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ነዳያንን የመደገፍ፣ አረጋውያንን የመንከባከብና ጧሪ ቀባሪ ያጡ ወገኖችን የመርዳት ተልእኮውን ቀጥሏል፡፡

መሥራቹ እንደ ገለጹልን ማኅበሩ ለዓላማው ማስፈጸሚያ የሚውለውን የገቢ ምንጭ የሚያገኘው ከአባላቱ ወርኃዊ መዋጮ፣ እንደዚሁም በአገር ውስጥና በውጭ አገር ከሚኖሩ በጎ አድራጊዎች ነው፡፡ በሒሳብ አያያዝም ዘመናዊና ሕጋዊ አሠራርን በመከተል ገቢውንና ወጪውን በደረሰኝ ይቈጣጠራል፤ ኦዲትም ያስደርጋል፡፡ የሚተዳደረውም በቦርድ አወቃቀር ሲኾን፣ ሕጋዊ ፈቃድና እውቅና አግኝቶ በበጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማኅበራት ኤጀንሲ ተመዝግቧል፡፡ የራሱ መተዳደርያ ደንብና ስልታዊ ዕቅድም አዘጋጅቷል፡፡ ወደፊት ለሚያከናውናቸው ተግባራትም ከፋይናንስና ኢኮኖሚ ልማት ቢሮ፣ ከሠራተኛና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ ጋር የፕሮጀክት ስምምነት ተፈራርሟል፡፡ ማኅበሩ ዘር፣ ሃይማኖት፣ ፆታ ሳይለይ ልዩ ርዳታ ለሚያስፈልጋቸው ሰዎች ከሠላሳ በላይ በሚኾኑ ሠራተኞቹ አማካይነት ድጋና ክብካቤ ያደርጋል፡፡ በዚህ ተግባሩ ባበረከተው አገራዊ አስተዋጽዖም በየጊዜው ከመንግሥትና ከሌሎች ልዩ ልዩ ተቋማት የምስጋና ገጸ በረከትና የሜዳልያ ሽልማት ተበርክቶለታል፡፡

የማኅበሩ ማእከል ውጫዊና ውስጣዊ ገጽታ በከፊል

ከጽ/ቤቱ ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተው ማኅበሩ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ እስከ ፳፻፰ ዓ.ም ድረስ ለስድስት መቶ ሃያ ሦስት ሰዎች የምግብ፣ የመጠለያና የሕክምና ድጋፍ አድርጓል፡፡ ከእነዚህ መካከል ሁለት መቶ አንዱ በማኅበሩ በተደረገላቸው ርዳታ ከሕመማቸው ተፈውሰዋል፡፡ አራቱ በማኅበሩ ውስጥ ተቀጥረው በማገልገል ላይ ሲኾኑ፣ ቀሪዎቹ ደግሞ በልዩ ልዩ የሥራ መስክ ተሰማርተው ራሳቸውን እያስተዳደሩ ነው፡፡ ሦስት መቶ ዐሥራ ሁለቱ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል፡፡ ማኅበሩ ካሁን በፊት ቤት ተከራይቶ አገልግሎት ሲሰጥ የቆየ ሲኾን፣ በአሁኑ ሰዓት ደግሞ በጉለሌ ክፍለ ከተማ ፈረንሳይ ለጋስዮን አንቀጸ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን አካባቢ ከመንግሥት በተሰጠው ቦታ ባስገነባው የአረጋውያን መጦርያና መንከባከቢያ በርካታ ሕሙማንንና አረጋውያንን አሰባስቦ የምግብ፣ የልብስ፣ የመጠለያና የሕክምና አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡ ከዚህ ዓለም በሞት የሚለዩትንም በክብር እንዲሸኙ ያደርጋል፡፡ በዚህ ዓመትም አገልግሎቱን በይበልጥ አጠናክሮ በከፍተኛ ባለሙያዎች በመታገዝ ከሦስት መቶ በላይ አረጋውያንን በማእከሉ በማሰባሰብ፤ ለሦስት መቶ አረጋውያን የተመላላሽና የቤት ለቤት ድጋፍ በማድረግ፤ እንደዚሁም ለአረጋውያኑና ለተንከባካቢዎቻቸው ልዩ ልዩ ሥልጠናዎችን በመስጠት የበጎ አድራጎት ተልእኮውን ሲወጣ ቆይቷል፤ ወደፊትም ይቀጥላል፡፡

ጕብኝት ባደረግንበት ወቅት እንዳስተዋልነው በማኅበሩ እየተጦሩ ከሚገኙ ወገኖች መካከል አንዳንዶቹ የአብነት መምህራን፣ የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች፣ በመንግሥትና በግል ድርጅቶች ሓላፊነት የነበራቸው ሰዎች ናቸው፡፡ እነዚህ የቤተ ክርስቲያንና የአገር ባለውለታዎች በሕመም፣ በጤና እና በእርጅና ምክንያት የአልጋ ቁራኛ፣ የደዌ ዳኛ ኾነው ጎዳና ላይ በወደቁበት ወቅት ይህ ማኅበር ደርሶላቸው አስፈላጊውን ዅሉ ድጋፍ እያደረገላቸው ይገኛል፡፡ በተለይ የአእምሮ ሕሙማንና ከአንድ በላይ በኾነ የጤና እክል የተጠቁ ማለትም የማየትም የመስማትም የመንቀሳቀስም ችግር ያለባቸውና ሰውነታቸውን መቈጣጠር የማይችሉ አባቶች፣ እናቶች፣ ወንድሞችና እኅቶች ኹኔታ ልብን ይነካል፡፡ እነዚህ ወገኖች የሚንቀሳቀሱትም፣ የሚመገቡትም፣ የሚለብሱትም፣ የሚጸዳዱትም በሰው ርዳታ ነው፡፡ እነርሱን ያየ ሰው የማኅበሩን ዓላማ በግልጽ ይረዳዋል የሚል እምነት አለን፡፡ የማኅበሩ መሥራች እንደ ነገሩን የሠራተኞችን ደመወዝ ሳይጨምር ለሕሙማኑ የዳይፐር መግዣ ብቻ በየቀኑ ከአንድ ሺሕ አራት መቶ ስልሳ አምስት ብር በላይ ወጪ ይደረጋል፡፡ ይህም ማኅበሩ ሰውን ለመርዳት ሲል የሚከፍለውን መሥዋዕትነትና የሚያሳልፈውን ውጣ ውረድ የሚያመለክት ነው፡፡

በማእከሉ ድጋፍ ከሚደረግላቸው ሕሙማንና አረጋውያን ጥቂቶቹ

በአጠቃላይ ‹‹መልካም ሥራ የክፉ ቀን ስንቅ ነው›› በሚለው መሪ ቃሉ የሚታወቀው የወደቁትን አንሡ የነዳያን መርጃ ማኅበር በጤና፣ በእርጅና ወይም በሌላ ልዩ ልዩ ምክንያት በየመንገዱ ወድቀው የሚለምኑ ወገኖችን በማሰባሰብ፤ እንደዚሁም በያሉበት ቦታ ባለሙያዎችን በመላክ የሕክምና፣ የምግብ እና የልብስ ድጋፍ እንዲያገኙ ያደርጋል፡፡ ለወደፊትም ይህን ተግባሩን በስፋት አጠናክሮ ለመቀጠል ዕቅድ አውጥቶ በመተግበር ላይ ነው፡፡ የማእከሉ ክሊኒክ በአካባቢው ለሚገኙ ድጋፍ ፈላጊ የኅብረተሰብ ክፍሎች የሕክምና አገልግሎት እንዲሰጥ ማድረግ፤ ተጨማሪ የመጠለያና የሆስፒታል ተቋማትን መገንባት፤ የጎዳና ላይ ምጽዋትን ተቋማዊ በማድረግ ነዳያን ወጥ በኾነ መንገድ ርዳታ እንዲያገኙ ማመቻቸት፤ ከርዳታ ድርጅቶችና በጎ አድራጎት ማኅበራት ጋር በጥምረት በመሥራት የአረጋውያንን ችግር በጋራ መፍታት ከማኅበሩ ዕቅዶች መካከል የሚጠቀሱ ተግባራት ናቸው፡፡

‹‹ስድስቱ ቃላተ ወንጌል በወደቁትን አንሡ የነዳያን መርጃ ማኅበር ውስጥ ይፈጸማሉ፤›› የሚሉት የማኅበሩ መሥራች አቶ ስንታየሁ አበጀ የየተቋማት ሠራተኞች፣ የድርጅት ባለቤቶች በጥቅሉ በጎ አድራጊ ወገኖች መጥተው ሕሙማኑን በመጠየቅና ቦታውን በመጐብኘት፣ የሚቻላቸው ደግሞ በምግብ፣ በቁሳቁስ (ልብስ፣ ፍራሽ፣ አልጋ፣ ወዘተ.) አቅርቦት እንደዚሁም የገንዘብ፣ የጉልበትና የሐሳብ ድጋፍ በማድረግ ቢተባበሩ የወደቁ ወገኖችን በማንሣት፣ ነዳያንን በመደገፍ፣ የታመሙትን በማሳከምና አረጋውያንን በመከንከባከብ ማኅበሩ ከዚህ ቀደሙ በበለጠ ሓላፊነቱን በአግባቡ ለመወጣት እንደሚቻለው አስረድተዋል፡፡ መሥራቹ እንደ ነገሩን ክርስትና፣ ሰርግ፣ ምረቃ፣ ተዝካርና የመሳሰሉ መርሐ ግብሮችን ማኅበሩ በሚያከራያቸው አዳራሾች ማዘጋጀት ደግሞ ሌላው የርዳታ ማድረጊያ መንገድ ነው፡፡ በመጨረሻም ላለፉት ዓመታት በልዩ ልዩ መንገድ ማኅበሩን በመደገፍ፤ እንደዚሁም ለትውልድ እንዲተላለፍ ኾኖ በታነጸው የአረጋውያን መጦርያ ማእከልና ክሊኒክ ግንባታ በመሳተፍ ላበረከተው አስተዋጽዖ አቶ ስንታየሁ ኅብረተሰቡን በእግዚአብሔር ስም አመስግነው፣ ‹‹ወደፊትም ማኅበሩ በሚያከናውናቸው ዘርፈ ብዙ ተግባራት ዓቅሙ በሚፈቅደው ዅሉ በመሳተፍ ኅብረተሰቡ ታሪካዊ አሻራውን እንዲያኖርና ወገናዊ ግዴታውን እንዲወጣ ይኹን›› ሲሉ በአረጋውያንና በዓቅመ ደካሞች ስም ጥሪ አቅርበዋል፡፡

አምላካችን በመንግሥቱ ያስበን ዘንድ ዅላችንም ከማኅበሩ ጋር በመኾን የወደቁትን እናንሣ የዝግጅት ክፍላችን መልእክት ነው፡፡ ማኅበሩን መደገፍ፣ በአባልነት መሳተፍ ወይም በመጦርያ ማእከሉ የሚገኙ ሕሙማንንና አረጋውያንን መጠየቅ ለምትፈልጉ የማእከሉ አድራሻ፡- አዲስ አበባ ከተማ የካ ክፍለ ከተማ ወረዳ 01 ፈረንሳይ ለጋስዮን ከገነተ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን 600 ሜትር ገባ ብሎ ራስ ካሣ በሚባለው ሰፈር ከአንቀጸ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን አጠገብ ነው፡፡ ስለ ማኅበሩ አገልግሎት የበለጠ መረጃ ለማግኘትም በሚከተሉት አድራሻዎች መጠየቅ ይቻላል፡፡

የቢሮ ስልክ ቍጥር፡- +251-111-243-401

አቶ ስንታየሁ አበጀ፡- 09 12 01 70 32 /09 35 99 92 92

ወ/ሮ ዓይናለም ኃይሌ፡- 09 11 23 91 59 /09 35 40 17 17

የፓስታ ሳጥን ቍጥር፡- 25404

E-mail፡- yewodekutnansu@gmail.com

aynalemamit@yahoo.com

Web site፡- www.yewedekutnansu.org

ገንዘብ በባንክ ገቢ ማድረግ የምትፈልጉ፣ የወደቁትን አንሡ የነዳያን መርጃ ማኅበር፡-

  1. በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መሐል ከተማ ቅርንጫፍ፣ የተንቀሳቃሽ ሒሳብ ቍጥር፡- 10000 0454 4513 ወይም 10000 2418 3959
  2. ኅብረት ባንክ ሒሳብ ቍጥር፡- 1141 1161 0272 1018 አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ብላችሁ እንድትልኩ ማኅበሩ ይጠይቃል፡፡ ገንዘቡ ወደ ባንክ ከገባ በኋላም ለሒሳብ ቍጥጥር ያመች ዘንድ በሦስት ኮፒ አሠርታችሁ አንዱን ኮፒ ለማኅበሩ እንድታደርሱ በአክብሮት ያሳስባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ዘመነ ክረምት – ክፍል አምስት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! በክፍል አራት ዝግጅታችን ከነሐሴ ፲ እስከ ፳፯ ቀን (ከማኅበር እስከ አብርሃም) ድረስ ያለው ሦስተኛው የዘመነ ክረምት ክፍለ ጊዜ (ንዑስ ክፍል) ‹ዕጕለ ቋዓት፣ ደሰያት፣ ዓይነ ኵሉ› እንደሚባል፤ ይኸውም የሰው ልጅ ብቻ ሳይኾን የሰማይ አዕዋፍ፣ የምድር አራዊትና እንስሳትም ጭምር እግዚአብሔርን አምነው በተስፋ መኖራቸው የሚዘከርበት፣ ደሴቶች በልምላሜ ማሸብረቃቸው የሚነገርበት ክፍለ ክረምት እንደ ኾነ፤ በቤተ ክርስቲያን የሚነገረው ቃለ እግዚአብሔርም በእነዚህ ምሥጢራት ላይ እንደሚያተኩር አስታውሰን፣ በተለይ ዕጕለ ቋዓትን መነሻ አድርገን ወቅቱን የሚመለከት ትምህርት አቅርበን ነበር፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን ደግሞ ባለፈ ካረፍንበት እንቀጥላለን፡፡ መልካም ንባብ! 

ደሰያት

በውኃ የተከበበ የብስ መሬት ‹ደሴት› ይባላል፤ ‹ደሰያት› ደግሞ ብዙ ቍጥርን አመላካች ቃል ነው፡፡ በዚህ ወቅት ስለ ደሴቶች በስፋት ይነገራል፡፡ ወቅቱ በድርቅ ብዛት የተጎዱ ደሴቶች በውኃ ብዛት የሚለመልሙበት፤ በውስጣቸው የሚኖሩ ሰዎች ብቻ ሳይኾኑ እንስሳትም አዕዋፍም ጭምር በሚበቅለው እኽልና በሚያገኙት ምግብ የሚደሰቱበት ጊዜ ነው፡፡ ደሴቶች በውኃ የተከበቡ የመሬት ክፍሎች እንደ መኾናቸው በዚህ ወቅት በልምላሜ ቢያጌጡም በማዕበልና በሞገድ መቸገራቸውም አይቀርም፡፡ ይህም የቤተ ክርስቲያን (የምእመናን ሕይወት) እና የዓለም ምሳሌ ነው፡፡ ደሴቶች በውኃ መከበባቸው ቤተ ክርስቲያን (የምእመናን ሕይወት) በክርስቶስ ደም የተመሠረተች፤ በቃለ እግዚአብሔር የታነጸች ለመኾኗ፤ ደሴቶች በማዕበልና በሞገድ መናወጣቸው ደግሞ በዓለም ውስጥ የሚከሠቱ ረኃብ፣ ጥላቻ፣ ጦርነት፣ ወዘተ የመሳሰሉ ችግሮች፤ በተለይ ሰይጣን የሚያመጣቸው ልዩ ልዩ ኅብረ ኃጢአት (የኀጢአት ዓይነቶች) የቤተ ክርስቲያንን (የምእመናንን) ህልውና የሚፈታተኑ መሰናክሎች መኾናቸውን ያጠይቃል፡፡

ይህቺ ዓለም፣ በውኃ የምትመሰል፣ ሞገድና ማዕበል የበዛባት ሥፍራ ናት፤ የክርስትና ሕይወት ደግሞ በውኃ የተከበበ መሬት፡፡ ውኃ በሞገድ፣ በማዕበል እንደሚናወጥ ዅሉ፣ ዓለምም በተፈጥሮም ይኹን በሰው ስሕተት በሚመጣ ኑፋቄ፣ ክህደት፣ መከራ፣ ችግር፣ ረኃብ፣ ጦርነት ትናወጣለች፤ ትንገላታለች፤ ትሰቃያለች፤ ትፈተናለች፡፡ ዛሬ በዓለም ላይ እየተፈጸመ ያለው ሰይጣናዊ ድርጊት ዅሉ ለዚህ ማስረጃ ነው፡፡ ዓለም ፈተና ላይ ናት፡፡ አልጠግብ ባይነት፣ ትምክህተኝነት፣ እኔ እበልጥ ባይነት፣ ፍቅር አልባነት (ጥላቻ)፣ ትዕቢት፣ ክህደት፣ ጥርጥር፣ ወዘተ የመሳሰሉ ችግሮች በነዋሪዎቿ ዘንድ እየተስፋፉ በመምጣታቸው ዓለም በፈተና ሞገድ እየተናወጠች ነው፡፡ እርሱ በቸርነቱ ሞገዱና ማዕበሉ ጸጥ እንዲል ካላደረገ የሰው ጥበብና ጥረት ብቻ ከዚህ ፈተና ዓለምን ሊያወጣት አይችልም፡፡ በውኃ የተከበበ መሬት ሞገድ፣ ማዕበልና ስጥመት እንደሚያጋጥመው ዅሉ፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም (የክርስትና ሕይወትም) በልዩ ልዩ መከራና ፈተና የታጀበ ነው፡፡ ምክንያቱም ክርስቲያኖች የምንኖረው ፈተና በሚያናውጣት ዓለም ወይም ውጣ ውረድ በበዛባት ምድር ላይ ነውና፡፡ ይኸውም ኀጢአት፣ ስደት፣ ኀዘን፣ ረኃብ፣ በሽታ፣ ጦርነት፣ ወዘተ. የመሳሰሉትን ምድራዊ ችግሮች ዅሉ ያካትታል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹እንዲህም ያለ መከራ በዓለም ባሉ ወንድሞቻችሁ ዅሉ እንደሚፈጸም ዕወቁ›› በማለት እንዳስተማረው (፩ኛ ጴጥ. ፭፥፱) በመላው ዓለም የሚኖሩ ክርስቲያኖች ዛሬ በመከራ ውስጥ ናቸው፡፡ በአንድ በኩል የዓለም የኑሮ ሸክም ከብዷቸው ይሰቃያሉ፤ በሌላ በኩል ደግሞ በአሕዛብና በአረማውያን ዛቻና ማስፈራሪያ ይጨነቃሉ፡፡ የክርስትና ትርጕም የገባቸውም በፈቃዳቸው በሰማዕትነት ይሞታሉ፡፡ ይህን ዅሉ ፈተና ተቋቁሞ በክርስትና ሃይማኖት ጸንቶ፣ በምግባር በርትቶ፣ በጸሎት ተግቶ የሚኖር ምእመን እርሱ ብፁዕ ነው፡፡ በሰማያዊው የእግዚአብሔር መንግሥት ለጻድቃን የተዘጋጀውን ሰላማዊና ዘለዓለማዊ ማረፊያ ይወርሳልና፡፡ እንግዲህ እኛም ሞገዱና ማዕበሉ ማለትም ምድራዊ ውጣ ውረዱና ፈተናው ቢያንገላታንም በዚህ ዓለም የሚጎድልብንን ሥጋዊው ጥቅምና የሚደርስብንን ጊዜያዊ መከራ ሳይኾን በእውነተኛው አገራችን በሰማይ የምንወርሰውን ዘለዓለማዊ መንግሥት ተስፋ በማድረግ ዅሉንም በጸጋ እንቀበል፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም ሃይማኖታችንንና ቤተ ክርስቲያናችንን ከልዩ ልዩ ፈተና ይጠብቅልን ዘንድም በፍጹም ሃይማኖት ኾነን እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹ከስጥመት አድነን?›› እያልን እግዚአብሔርን በጸሎት እንጠይቀው፡፡ እርሱ በባሕር፣ በሞገድ፣ በማዕበልና በነፋስ የሚመሰለውን የዓለምን ውጣ ውረድና መከራ መገሠፅ፤ ሁከቱንም ጸጥ ማድረግ የሚቻለው አምላክ ነውና (ማቴ. ፰፥፳፫-፳፯)፡፡ ከዓቅማችን በላይ የኾነ ችግር ሲያጋጥመን ደግሞ የሚያስጨንቀንን ጉዳይ ዅሉ ለእርሱ ለፈጣሪያችን እንስጠው፡፡ ይህን ለመወሰን እንዲቻለንም የሚከተለውን የመጽሐፍ ቅዱስ ኃይለ ቃል እናስተውል፤ ‹‹እንግዲህ በጐበኛችሁ ጊዜ ከፍ ከፍ ያደርጋችሁ ዘንድ ከጸናችው ከእግዚአብሔር ክንድ በታች ራሳችሁን አዋርዱ፡፡ እርሱ ስለ እናንተ ያስባልና የሚያስጨንቃችሁን ዅሉ በእርሱ ላይ ጣሉት፡፡ እንግዲህ ዐዋቂዎች ኹኑ፤ ትጉም፡፡ ጠላታችሁ ጋኔን የሚውጠውን ፈልጎ፣ እንደሚያገሳ አንበሳ ይዞራልና፡፡ እርሱንም በእምነት ጸንታችሁ ተቃወሙት፤ እንዲህም ያለ መከራ በዓለም ባሉ ወንድሞቻችሁ ዅሉ እንደሚፈጸም ዕወቁ፡፡ ፍቅርንም አጽንታችሁ ያዙአት፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዘለዓለም ክብሩ የጠራችሁ የጸጋ ዅሉ አምላክ ለጥቂት ጊዜ መከራን ከተቀበላችሁ በኋላ ፍጹማን ያደርጋችኋል፤ ያጸናችኋል፤ ልባሞችም ያደርጋችኋል፤›› (፩ኛ ጴጥ. ፭፥፮-፲)፡፡

ዓይነ ኵሉ

‹ዓይነ ኵሉ› ትርጕሙ በግእዝ ቋንቋ ‹የዅሉም ዓይን› ማለት ነው፡፡ ይህ ወቅት ያለፈው (በበጋ የነበረው) እኽል ከሪቅ፣ ከጎተራ ያለቀበት፤ የተዘራውም ያላፈራበት ገና የተክል ጊዜ ነው፡፡ ፍጥረታት በሙሉ የፍሬውን ሰዓት በተስፋ የሚጠባበቁበት ክፍለ ክረምት ስለ ኾነ ወቅቱ ‹ዓይነ ኵሉ› ተብሏል፡፡ ይኸውም ፍጥረታት ዅሉ ወደ ፈጣሪያቸው ወደ እግዚአብሔር በማንጋጠጥ የዕለት ጕርስ፣ የዓመት ልብስ እንዳይከለክላቸው እንደሚማጸኑና ዘወትር የእርሱን መግቦት ተስፋ አድርገው እንደሚኖሩ የሚያስረዳ ቃል ነው፡፡ ‹‹ዐይነ ኵሉ ነፍስ ይሴፎ ኪያከ አንተ ትሁቦሙ ሲሳዮሙ በጊዜሁ ትሰፍሕ የማነከ ወታጸግብ ለኵሉ እንስሳ ዘበሥርዓትከ፤ የሰው ዅሉ ዓይን አንተን ተስፋ ያደርጋል፤ አንተም ምግባቸውን በየጊዜው ትሰጣቸዋለህ፡፡ ቀኝ እጅህን ትዘረጋለህ፤ በሥርዓትህ ለሚኖሩ እንስሳት ዅሉ ታጠግባለህ፤›› እንዳለ ቅዱስ ዳዊት (መዝ. ፻፵፬፥፲፭-፲፮)፡፡ ይኸውም የሰው ልጅ ዅሉ (ዓይን የተባለ ሰውነት ነው) እግዚአብሔርን ተስፋ አድርጎ እንደሚኖር፤ እርሱም በዘር ጊዜ ዘሩን፣ በመከር ጊዜ መከሩን፣ በበልግ ጊዜ በልጉን እያዘጋጀ በየጊዜው ምግባቸውን እንደሚሰጣቸው፤ እንደዚሁም እግዚአብሔር ለሰው ልጅ ብቻ ሳይኾን በሰፊው እጁ (በማያልቅ ቸርነቱ) በሥርዓቱ ጸንተው ለሚኖሩ ለእንስሳት ጭምር ምግባቸውን እየሰጠ ደስ እንደሚያሰኛቸው የሚያስረዳ ኃይለ ቃል ነው፡፡

የቤተ ክርስቲያናችን መተርጕማን እንደሚያትቱት ከሰው ልጅ በቀር ከእግዚአብሔር ሥርዓት የወጣ እንስሳ የለም፤ ማለትም ሰው እንጂ እንስሳት ሕገ እግዚአብሔርን አልተላለፉም፡፡ ነገር ግን የሰው ልጅ አምላክነትን ተመኝቶ ‹‹አትብላ›› የተባለውን ዕፅ በመብላት ሕጉን፣ ትእዛዙን ተላልፏል፡፡ እግዚአብሔርም ይቅር ባይ አምላክ ነውና የሰውን ልጅ (የአዳምን) ንስሐ ተመልክቶ፣ ኀጢአቱን ይቅር ብሎ ሞቱን በሞቱ ሽሮ አድኖታል፡፡ እግዚአብሔር አምላችን በፍጡራኑ የማይጨክን፤ የለመኑትን የማይነሳ፤ የነገሩትንም የማይረሳ አምላክ መኾኑን በማስተዋልና ቸርነቱን ተስፋ በማድረግ በምድር በረከቱን እንዲሰጠን፤ ቅዱስ ሥጋውን ለመብላት፣ ክቡር ደሙን ለመጠጣ እንዲያበቃን፤ በሰማይም ዘለዓለማዊ መንግሥቱን እንዲያወርሰን እኛም በንጹሕ ልብ ኾነን ዘወትር ልንማጸነው ይገባናል፡፡ በሰው ከመታመን ይልቅ በእግዚአብሔር መታመን ይበልጣልና (መዝ. ፻፲፯፥፰)፡፡ ደግሞም ‹‹አንተን ተስፋ የሚያደርጉ አያፍሩም›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (መዝ. ፳፬፥፫) እግዚአብሔርን ተስፋ ማድረግ አያሳፍርምና፡፡

ይቆየን

ፅንሰተ ማርያም ድንግል

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከተወደደ ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ ነሐሴ ሰባት ቀን ከሚዘከሩ በዓላት መካከል የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ፅንሰት አንደኛው ነው፡፡ በዓሉን ለመዘከር ያህልም የእመቤታችንን የመፀነስ ታሪክ በአጭሩ እናስታውሳችሁ፤

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቅድመ አያቶች ቴክታ እና በጥሪቃ ይህ ቀራቸው የማይባሉ ባለ ጠጎች ነበሩ፡፡ ነገር ግን መካኖች ነበሩ፡፡ ዘራቸውን ባለመተካታቸውና ሀብታቸውን የሚወርስ ልጅ ባለማግኘታቸውም ያዝኑ፣ ይተክዙ ነበር፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን በጥሪቃ ሚስቱ ቴክታን ጠርቶ ‹‹አንቺ መካን፤ እኔ መካን፡፡ ይህ ገንዘብ ለማን ይኾናል?›› አላት፡፡ ቴክታም ‹‹እግዚአብሔር ከእኔ ልጅ ባይሰጥህ ከሌላ ይሰጥህ ይኾናል፡፡ ሌላ ሚስት አግብተህ ልጅ አትወልድምን?›› አለችው፡፡ እርሱም ‹‹ይህንስ እንዳላደርገው አምላከ እስራኤል ያውቃል›› አላት፡፡ በዚህ አኳኋን እያዘኑ ሲኖሩ አንድ ቀን ነጭ እንቦሳ (ጥጃ) ከበረታቸው ስትወጣ፤ እንቦሳይቱ እንቦሳ እየወለደች እስከ ስድስት ልጅ ስትደርስና ስድስተኛዪቱ እንቦሳም ጨረቃን፣ ጨረቃም ፀሐይን ስትወልድ ራእይ አዩ፡፡

ራእያቸውን ለሕልም ተርጓሚ ሲነግሩም ‹‹የጨረቃዪቱ ትርጕም ከፍጡራን በላይ የምትኾን ልጅ እንደምታገኙ የሚያመለክት ነው፡፡ የፀሐይ ነገር ግን አልተገለጠልኝም፡፡ እንደ ነቢይ፣ እንደ ንጉሥ ያለ ይኾናል፤›› አላቸው፡፡ እነርሱም ይህን ሲሰሙ ‹‹ጊዜ ይተርጕመው ብለው›› ወደ ቤታቸው ተመለሱ፡፡ ከዚህ በኋላ እግዚአብሔር ጸሎታቸውን ሰምቶ ለዘር ሊያበቃቸው ፈቅዷልና መካኗ ቴክታ ፀንሳ ሴት ልጅ ወለደች፤ ስሟንም ‹ሄኤሜን› አለቻት፡፡ ትርጕሙም ‹ስእለቴን (ምኞቴን) አገኘሁ› ማለት ነው፡፡ ሄኤሜንም ለዓቅመ ሔዋን ስትደርስ ዴርዴን፤ ዴርዴ ቶናን፤ ቶና ሲካርን፤ ሲካር ሄርሜላን፤ ሄርሜላ ሐናን ወለዱ፡፡ ለሐናም ኢያቄም ለሚባል ደግ ሰው አጋቧት፡፡ እነርሱም እንደ በጥሪቃና ቴክታ መካኖች ኾኑ፡፡

በእስራኤላውያን ባህል መካንነት የእርግማን ምልክት ተደርጎ ይቈጠር ነበርና ሐና እና ኢያቄም ብዙ ዘለፋና ሽሙጥ ይደርስባቸው ነበር፡፡ በአንድ ወቅት መሥዋዕት ለማቅረብ ወደ ቤተ መቅደስ ሔዱ፡፡ የዘመኑ ሊቀ ካህናት ሮቤል መካን መኾናቸውን ያውቅ ነበርና ‹‹እናንተማብዙ ተባዙብሎ እግዚአብሔር ለአዳም የነገረውን ቃል ያስቀረባችሁ ርጉማን አይደላችሁምን? እግዚአብሔር ቢጠላችሁ እንጂ ቢወዳችሁማ ልጅ ይሰጣችሁ አልነበረምን?›› ብሎ መሥዋዕታቸውን ሳይቀበላቸው ቀረ፡፡ አንድም ከአዕሩገ እስራኤል (ከአረጋውያን እስራኤላውያን) የተወለዱ ሰዎች የሚመገቡትን ተረፈ መሥዋዕት እንዳይመገቡ ከለከላቸው፡፡ በዚህ እያዘኑ ሲመለሱ ከመንገድ ላይ ከልጆቻቸው ጋር የሚጫወቱ ርግቦችንና አብበው ያፈሩ ዕፀዋትን ሐና ተመለከተች፡፡ እርሷም ‹‹ርግቦችን በባሕርያቸው መራባት እንዲችሉ፤ ዕፀዋትንአብበው እንዲያፈሩ የምታደርግ ጌታ እኔን ለምን ልጅ ነሳኸኝ?›› ብላ አዘነች፡፡

ከቤታቸው ሲደርሱም ‹‹እግዚአብሔር ልጅ ቢሰጠን ወንድ ከኾነ ለቤተ እግዚአብሔር ምንጣፍ አንጣፊ፣ መጋረጃ ጋራጅ ኾኖ ሲያገለግል ይኑር፤ ሴት ብትኾንም መሶበ ወርቅ ሰፍታ፣ መጋረጃ ፈትላ ስታገለግል ትኑር›› ብለው ተሳሉ፡፡ ከዚህ በኋላ ሐምሌ ፴ ቀን ኹለቱም ራእይ አዩ፡፡ ሐና ‹‹በሕልሜ ፀምር (መጋረጃ) ሲያስታጥቁህ፤ በትርህ አፍርታ ፍጥረት ሲመገባት አየሁ›› ብላ ያየቸውን ራእይ ለኢያቄም ነገረችው፡፡ ኢያቄምም ‹‹ጸዓዳ ርግብ ሰባቱን ሰማያት ሰንጥቃ መጥታ በራስሽ ላይ ስታርፍ፣ በቀኝ ጆሮሽ ገብታ በማኅፀንሽ ስታድር አየሁ›› ብሎ ያየውን ራእይ ለሐና ነገራት፡፡ ወደ ሕልም ተርጓሚ ሔደው ትርጕሙን ሲጠይቁም ‹‹ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹አንተ አልፈታኸውም፤ ጊዜ ይፍታው›› ብለው ተመለሱ፡፡ በሌላ ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ‹‹ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ›› ብሎ የሕልሙን ትርጕም ትክክለኛነት ነግሯቸዋል፡፡

ከዚህ በኋላ ብሉይ ኪዳን (ዓመተ ዓለም፣ ዓመተ ፍዳ) ተፈጽሞ የሐዲስ ኪዳን መግባት ሊበሠር፤ ጌታችንም ሊፀነስ ፲፬ ያህል ዓመታት ሲቀሩ በፈቃደ እግዚአብሔር ነሐሴ ፯ ቀን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተፀንሳለች፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በእናቷ በቅድስት ሐና ማኅፀን ሳለች ካደረገቻቸው ተአምራት መካከልም በርሴባ የምትባል ሴትን ዓይን ማብራቷ አንደኛው ነው፡፡ ይህቺ አንድ ዓይና ሴት (በርሴባ) ‹‹እግዚአብሔር በረድኤት ጐበኘሽ መሰለኝ፤ ጡቶችሽ ጠቁረዋል፤ ከንፈሮችሽ አረዋል›› ብላ የሐናን ማኅፀን በዳሰሰችበት እጇ ብታሻሸው ዓይኗ በርቶላታል፡፡

ይህንን አብነት አድርገውም እንደ እርሷ የሐናን ማኅፀን በመዳሰስ ብዙ ሕሙማን ከደዌያቸው ተፈውሰዋል፡፡ እንደዚሁም ሳምናስ የሚባል ልጅ በሞተ ጊዜ ሐና የአልጋውን ሸንኮር ይዛ ስታለቅስ ጥላዋ ቢያርፍበት ከሞት ተነሥቶ ‹‹ሰላም ለኪ እምሔውቱ ለዘገብረ ሰማየ ወምድረ፤ ሰማይና ምድርን የፈጠረው አምላክ አያቱ ሐና ሆይ! ሰላም ላንቺ ይኹን! ሰላምታ ይገባሻል!›› በማለት ሕልም ተርጓሚ ያልፈታውን ራእይ በመተርጐም ከቅድስት ሐና እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፤ ከእመቤታችን ደግሞ እውነተኛው ፀሐይ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንሚወለድ አስቀድሞ ተናግሯል፡፡

በአጠቃላይ ‹‹ቀደሰ ማኅደሮ ልዑል ልዑል እግዚአብሔር ማደሪያውን መረጠ፤ አከበረ፤ ለየ፤ ቀደሰ …፤›› (መዝ. ፵፭፥፬) በማለት ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ እንደ ተናገረው፣ አምላክን ለመውለድ የተመረጠችው ማኅደረ ማለኮት፤ የዓለሙን ቤዛ በመውለዷ ‹‹ቤዛዊተ ዓለም›› እየተባለች የምትጠራው፤ በአምላክ ሕሊና ታስባ ትኖር የነበረችው፤ የድኅነታችን ምክንያት የኾነችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በማኅፀን የተቋጠረችው (የተፀነሰችው) ነሐሴ ፯ ቀን ነው፡፡ ፅንሰቷም እግዚአብሔር በባረከውና ባከበረው ቅዱስ ጋብቻ በተወሰኑት ወላጆቿ በቅዱስ ኢያቄምና በቅድስት ሐና ሥርዓት ያለው ግንኙነት ነው፡፡ ‹‹ ድንግል አኮ በፍትወተ ደነስ ዘተፀነስኪ አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ፤ ድንግል ሆይ በሥጋዊ ፈቃድ የተፀንሽ አይደለሽም፤ ሕጋዊ በኾነ ሥርዓት ከሐና እና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጂ፤›› እንዳሉ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴ ማርያም፡፡

ስለዚህም ‹‹ ማርያም በእንተዝ ናፈቅረኪ ወናዓብየኪ እስመ ወለድኪ ለነ መብልዐ ጽድቅ ዘበአማን ወስቴ ሕይወት ዘበአማን፤ ማርያም ሆይ! እውነተኛውን ምግብ፣ እውነተኛውን መጠጥ አስገኝተሽልናልና እናከብርሻለን፤ እናገንሻለን፤›› በማለት አባ ሕርያቆስ እንዳመሰገኗት፣ ዘለዓለማዊ ሕይወት የሚሰጠውን፤ ከሞተ ሥጋ ከሞተ ነፍስ ማዳን የሚቻለውን፤ እውነተኛውን ምግበ ሥጋ ወነፍስ ኢየሱስ ክርስቶስን ስለ ወለደችልን ‹‹እናታችን፣ እመቤታችን፣ አማላጃችን፣ የድኅነታችን ምክንያት፣ ወዘተ›› እያልን ቅድስት ድንግል ማርያምን እናከብራታለን፤ እናገናታለን፤ እናመሰግናታለን፡፡ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በረከት አይለየን፡፡ እናቱን በአማላጅነት፤ ራሱን በቤዛነት ለሰጠን ለልዑል እግዚአብሔር ክብር፣ ምስጋና ይድረሰው፡፡

ምንጭ፡ቅዳሴ ማርያም አንድምታ ትርጓሜ፣ ፭፥፴፰፡፡

ተስእሎተ ቂሣርያ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፮ ቀን ፳፻፱ .

በየዓመቱ ነሐሴ ፯ ቀን በቤተ ክርስቲያናችን ከሚከበሩ የጌታችን በዓላት መካከል የተስእሎተ ቂሣርያ በዓል አንደኛው ነው፡፡ ‹ተስእሎተ ቂሣርያ›፣ የቃሉ (ሐረጉ) ትርጕም ‹በቂሣርያ አገር የቀረበ ጥያቄ› ማለት ሲኾን፣ ይኸውም ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ሰዎች ማን ይሉኛል?›› ብሎ ደቀ መዛሙርቱን መጠየቁን ያስረዳል፡፡ በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈው ጌታችን በቂሣርያ አውራጃ ሐዋርያቱን ሰብስቦ ‹‹ሰዎች የሰውን ልጅ (ኢየሱስ ክርስቶስን) ማን ይሉታል?›› ብሎ ሲጠይቃቸው እነርሱም ‹‹ዮሐንስ፣ ኤልያስ፣ ኤርምያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው ይላሉ›› የሚል ምላሽ ሰጥተውታል፡፡ እርሱም መልሶ ‹‹እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ?›› የሚል ጥያቄ ባቀረበላቸው ጊዜ የሐዋርያት አለቃ ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹አንተ ውእቱ ክርስቶስ ወልደ እግዚአብሔር ሕያው፤ አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ›› ብሎ የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት የሚያስረዳ ምላሽ ሰጥቷል፡፡ የቅዱስ ጴጥሮስ ምላሽም ሰዎች ስለ ክርስቶስ ማንነት ከሚሰጡት ግምትና ከሐዋርያት ዕውቀት በላይ በመኾኑ ጌታችን ‹‹የእኔን አምላክነት ሰማያዊ አባቴ ገለጸልህ እንጂ ሥጋዊ ደማዊ አእምሮ አልገለጸልህም›› በማለት በአንክሮ ተቀብሎታል፡፡

ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰዎች ስለ እርሱ የሚናገሩትንም፣ የሚያስቡትንም የሚያውቅ አምላክ ሲኾን በቂሣርያ ሐዋርያቱን ‹‹ሰዎች ማን ይሉኛል›› ብሎ መጠየቁ በአንድ በኩል አላዋቂ ሥጋን መልበሱን ለማጠየቅ፤ በሌላ ምሥጢር ደግሞ አምላክነቱን ለመግለጥ፣ እንደዚሁም መዓርገ ክህነትን ለሐዋርያትና ለተከታዮቻቸው (ለጳጳሳት፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት) ለመስጠት ነው፡፡ ይህም በቅዱስ ጴጥሮስ ምላሽና ጌታችን በሰጠው ሥልጣን ይታወቃል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ስለ ክርስቶስ የእግዚአብሔር አብ ልጅነትና የባሕርይ አምላክነት ከመሰከረ በኋላ ጌታችን፣ ‹‹አንተ ዓለት (መሠረት) ነህ፤ በአንተ መሠረትነት ቤተ ክርስቲያኔን እሠራታለሁ፡፡ የገሃነም ደጆች (አጋንንት) አይችሏትም፡፡ የመንግሥተ ሰማያትን መክፈቻ እሰጥሃለሁ፡፡ በምድር ያሠርኸው በሰማይም የታሠረ፤ በምድር የፈታኸው በሰማይም የተፈታ ይኾናል›› በማለት ለአብያተ ክርስቲያናት መስፋፋት፣ ለስብከተ ወንጌል አገልግሎትና ለምእመናን ድኅነት ምክንያት የኾነውን መዓርገ ክህነት ሰጥቶታል (ማቴ. ፲፮፥፲፫-፲፱)፡፡

ይህ ሥልጣነ ክህነት በቅዱስ ጴጥሮስ አንጻር ከሐዋርያት ጀምሮ ለሚነሡ አባቶች ካህናት የተሰጠ ሰማያዊ ሀብት ነው፡፡ ዛሬ ምእመናን በኃጢአት ስንወድቅ ከካህናት ፊት ቀርበን የምንናዘዘውና ንስሐ የምንቀበለው፤ በመስቀሉ እየተባረክን ‹‹ይፍቱን›› የምንለው ጌታችን ለሐዋርያት የሰጣቸውን ሥልጣነ ክህነት መሠረት በማድረግ ነው፡፡ አባቶች ካህናትም ‹‹ይኅድግ ይፍታሕ ያንጽሕ ወይቀድስ …›› እያሉ በመናዘዝ ‹‹እግዚአብሔር ይፍታ›› የሚሉን ከባለቤቱ የማሠርና የመፍታት ሥልጣን ስለ ተሰጣቸው ነው፡፡

ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በትርጓሜያቸው እንደሚያስረዱት ጌታችን ሐዋርያቱን ‹‹እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ?›› ብሎ ከጠየቃቸው በኋላ ምላሻቸውን ተከትሎ ሥልጣነ ክህነትን መስጠቱ በብሉይ ኪዳን (እግዚአብሔር አምላክ በሥጋ ከመገለጡ በፊት) አዳም የት እንዳለ እያወቀ ‹‹አዳም ሆይ ወዴት ነህ?›› (ዘፍ. ፫፥፲) ብሎ ከጠየቀውና ያለበትን እንዲናገር ካደረገው በኋላ ‹‹ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ›› የሚል የድኅንት ቃል ኪዳን መግባቱን ያስታውሰናል፡፡ እግዚአብሔር በሦስትነቱ ከአብርሃም ቤት በገባ ጊዜ ሣራ ያለችበትን ቦታ እያወቀ ‹‹ሚስትህ ሣራ ወዴት ናት?›› ሲል አብርሃምን ያለችበትን ቦታ እንዲናገር ካደረገው በኋላ ‹‹ሣራ ልጅን ታገኛለች›› የሚል ቃል መናገሩም ከዚህ ትምህርት ጋር ተመሳሳይነት አለው፡፡ ቃሉም በአንድ በኩል የይስሐቅን መወለድ፤ በሌላ በኩል ደግሞ የእግዚአብሔርን ሰው መኾንና የሐዲስ ኪዳንን መመሥረት የሚያጠይቅ ነው (ዘፍ. ፲፰፥፱-፲፭)፡፡

በሐዲስ ኪዳንም አልዓዛር በሞተ ጊዜ ጌታችን የተቀበረበትን ቦታ እያወቀ ‹‹አልዓዛርን ወዴት ቀበራችሁት›› ብሎ መካነ መቃብሩን ከጠየቀ በኋላ በሥልጣኑ ከሞት እንዲነሣ ማድረጉም ከተስእሎተ ቂሣርያ እና ከላይ ከጠቀስናቸው ምሳሌዎች ጋር የሚወራረስ ምሥጢር አለው (ዮሐ. ፲፩፥፴፯)፡፡ ይኼ ዅሉ ቃል እግዚአብሔር አምላክ ሐሳባቸውን ያላወቀ መስሎ እየጠየቀ ሰዎች ስሜታቸውን እንዲገልጡ እንደሚያደርግ፤ የልባቸውን መሻትና እምነት መሠረት አድርጎም ሥልጣንን፣ በረከትን፣ ጸጋንና ፈውስን እንደሚያድላቸው የሚያስረዳ ትምህርት ነው፡፡ ለዚህም ጌታችን በመዋዕለ ሥጋዌው በአካለ ሥጋ ሲመላለስ መዳን እንደሚፈልጉ እያወቀ ‹‹ልትድን ትወዳለህን? ልትድኚ ትወጃለሽን? ልትድኑ ትወዳላችሁን?›› ብሎ እየጠየቀ የልባቸውን መሻት እንዲናገሩ ካደረገ በኋላ የእምነታቸውን ጽናት አይቶ በአምላካዊ ቃሉ ‹‹ፈቀድኩ ንጻሕ፤ ፈቀድኩ ንጽሒ፤ ፈቀድኩ ንጽሑ = ፈቅጃለሁ ተፈወስ፤ ፈቅጃለሁ ተፈወሺ፤ ፈቅጃለሁ ተፈወሱ፤›› እያለ ለሕሙማነ ሥጋ ወነፍስ ፈውስን ማደሉ ትልቅ ማስረጃ ነው፡፡

ትምህርቱን ወደ እኛ ሕይወት ስናመጣው ዛሬ ዓለም ክርስቶስን ማን ትለዋች? እኛስ ማን ብለን እንጠራዋለን? ምላሹ እንደየሰዉ የመረዳት ዓቅም ሊለያይ ይችላል፡፡ እውነታው ግን አንድ ብቻ ነው፤ በእርግጥ እግዚአብሔር አምላክ ከሰማየ ሰማያት ወርዶ፣ ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ ሕዝቡን እንዳዳነ ያልገባት ዓለም ክርስቶስን ከፍጡራን ተርታ ትመድበዋለች፡፡ የእርሷ የፍልስፍና ሐሳብ አራማጆች መናፍቃንም አምላክነቱን ክደው ‹‹አማላጅ ነው›› ይሉታል (ሎቱ ስብሐት)፡፡ ሌሎችም እንደየዓቅማቸው ለክብሩ በማይመጥን ልዩ ልዩ ስም ይጠሩታል፡፡ በሐሰተኛ ትምህርታቸውም ብዙ የዋሃንን አሰናክለዋል፡፡ እርሱ ባወቀ ወደ ቤቱ ይመልሳቸው እንጂ፡፡ እኛ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ልጆች ግን እርሱ ባለቤቱ፣ ቅዱሳን ሐዋርያትና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንዳስተማሩን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሦስቱ አካላት አንዱ፤ የእግዚአብሔር ልጅ እግዚአብሔር (አምላክ ወልደ አምላክ)፤ በቈረሰው ሥጋ፣ ባፈሰሰው ደሙ ከዘለዓለማዊ ሞት ያዳነን የዅላችን ቤዛ እንደ ኾነ እናምናለን፤ እንታመናለን፡፡ ይህን ሃይማኖታችንንም ለዓለም በግልጽ እንመሰክራለን፡፡ እርሱም በምድር እንደየእምነታችን መጠን መንፈሳዊ ጸጋን፣ በረከትን፣ ፈውስን ያድለናል፡፡ በሰማይም እንደየሥራችን ዋጋ ይከፍለናል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን እንደ እኛ ድክመት ሳይኾን እንደ ቸርነቱ ብዛት ስሙን ለመቀደስ፤ መንግሥቱንም ለመውረስ ያብቃን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ሱባዔና ሥርዓቱ – ክፍል ሦስት (የመጨረሻ ክፍል)

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

ነሐሴ ፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ሱባዔ በዘመነ ሐዲስ

በዘመነ ሐዲስ በሰፊው የሚወሳው ሱባዔ ቅዱሳን ሐዋርያት ከነሐሴ ፩ – ፲፬ ቀን ድረስ የገቡት ሱባዔ ነው፡፡ ይህ ሱባዔ ተሰውሮ የነበረውን የቅድስት ድንግል ማርያምን ትንሣኤ ተረድተው በረከቷን ለመሳተፍ አብቅቷቸዋል፡፡ እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሦስት ዓመት በእናት በአባቷ ቤት፣ ዐሥራ ሁለት ዓመት በቤተ መቅደስ፣ ሠላሳ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ከጌታችን ጋር፣ ዐሥራ አምስት ዓመት በወንጌላዊው በዮሐንስ ቤት ከኖረች በኋላ በ፷፬ ዓመቷ ጥር ፳፩  ቀን ዐርፋለች፡፡ በሐዋርያት ውዳሴ፣ ዝማሬና ማኅሌት ነሐሴ ፲፬ ቀን ከተቀበረች በኋላ ነሐሴ ፲፮ ተነሥታ በይባቤ መላእክት ወደ ሰማይ ዐርጋለች፡፡ ቅዱስ ያሬድ በመዝሙሩ ‹‹ተለዐለት እምድር ወበህየ ነበረት ዘምስለ ወልዳ በየማነ አብ ወመንፈስ ቅዱስ፤ እመቤታችን ድንግል ማርያም ከምድር ወደ ሰማይ ዐረገች፡፡ በሰማይም ከልጅዋ ጋር በአብና በመንፈስ ቅዱስ ቀኝ ተቀመጠች፤›› በማለት ወደ ሰማይ ማረጓንና በክብር መቀመጧን ተናግሯል፡፡ ከሺሕ ዓመት በፊትም አባቷ ዳዊት ‹‹በወርቅ ልብስ ተጐናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች›› ሲል የተናገረው ትንቢት ይህንኑ የእመቤታችንን ክብር የሚመለከት ነው (መዝ. ፵፬፥፱)፡፡

‹ፍልሰት› የሚለው ቃል የእመቤታችን ሥጋ ከጌቴሴማኒ ወደ ገነት መፍለሱን፣ በኋላም በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር ከነበረበት መነሣቱን ለማመልከት የሚነገር ነው (ወላዲተ አምላክ በኢትዮጵያ፣ ገጽ 68)፡፡ ለሐዋርያት የእመቤታችን የዕረፍትና የዕርገት ምሥጢር የተገለጠላቸው በሱባዔ ነው፡፡ ይህን መሠረት በማድረግ በየዓመቱ ጾመ ፍልሰታ ወይም የሐዋርያት ሱባዔ ከሊቅ እስከ ደቂቅ በቤተ ክርስቲያን ይታሰባል፡፡ ምእመናን የተቻላቸው ከሰው ርቀው፣ ሱባዔ ገብተው፣ ያልተቻላቸው ደግሞ በአጥቢያቸው የውዳሴዋና የቅዳሴዋን ትርጕም ይሰማሉ፤ በሰዓታቱና በቅዳሴው ሥርዓት ይሳተፋሉ፡፡ በእመቤታችን አማላጅነት፣ በልጇ ቸርነት በምድር ሳሉ በሃይማኖት ጸንተው ለመኖር፤ በኋላም ለመንግሥቱ እንዲያበቃቸው እግዚአብሔርን ደጅ ይጠናሉ፡፡

የሱባዔ ዓይነቶች

፩. የግል ሱባዔ (ዝግ ሱባዔ)

የግል ሱባዔ አንድ ሰው ብቻውን ኾኖ በቤትና በአመቺ ቦታ የሚይዘው ማንም ሰው ሳያየው በግሉ የጸሎት በዓቱን ዘግቶ በሰቂለ ሕሊና ኾኖ ፈጣሪው ብቻ እንዲያየውና እንዲሰማው በኅቡዕ የሚፈጽመው ሱባዔ ነው (ማቴ. ፮፥፭-፲፫)፡፡ በዚህ ዓይነት መንገድ አንድ ሰው ሱባዔ ሲገባ ዘጋ ይባላል፡፡ ዝግ ሱባዔ የያዘ ሰው የሚያስፈልገውን ነገር ይዞ ወደ በዓቱ ከተከተተ በኋላ ሱባዔው እስኪፈጸም ድረስ ከሰው አይገናኝም (መዝ. ፻፩፥፮-፯)፡፡

፪. የማኅበር ሱባዔ

የማኅበር ሱባዔ የሚባለው ካህናት፣ ምእመናን ወንዶችና ሴቶች፣ ሽማግሌዎችና ወጣቶች በአንድነት ኾነው በቤተ ክርስቲያንና አመቺ በኾኑ ቦታዎች ዅሉ ተሰባስበው የሚገቡት ሱባዔ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን የነበሩ ምእመናን ወደ እግዚአብሔር ቤት በመሔድ ይጸልዩ ነበር (፩ኛ ሳሙ. ፩፥፩፤ መዝ. ፻፳፩፥፩፤ ሉቃ. ፲፰፥፲-፲፬)፡፡ በሐዲስ ኪዳንም የሐዋርያት ተከታዮች የኾኑ መነኮሳት፣ ካህናትና ምእመናን በገዳማት፣ በአድባራት፤ የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች፣ የጽዋ ማኅበርተኞች ስለ ማኅበራቸው ጥንካሬና ከማኅበርተኞቹ መካከል አንዱ ችግር ሲገጥመው የማኅበር ሱባዔ ይይዛሉ፡፡

፫. የዐዋጅ ሱባዔ

የዐዋጅ ሱባዔ በአገር ላይ ድንገተኛ አደጋ፣ አባር ቸነፈርና ጦርነት ሲከሠት፤ እንደዚሁም ለማኅበረ ምእመናን አስጊ የኾነ መቅሠፍት ሲመጣ፤ እግዚአብሔር መዓቱን በምሕረት፣ ቍጣውን በትዕግሥት እንዲመልስ የሚያዝ የሱባዔ ዓይነት ነው፡፡ ለዚህ ዓይነቱ ሱባዔ የነነዌ ሰዎችና በፋርስ በስደት ይኖሩ የነበሩ እስራኤላውያን ምሳሌዎች ናቸው፡፡ የነነዌ ሰዎች የዮናስን ስብከት ሰምተው ከሊቅ እስከ ደቂቅ ድረስ ለሦስት ቀናት ከመብል ከመጠጥ ተከልክለው በመጾም በመጸለያቸው እግዚአብሔር መዓቱን በምሕረት፣ ቍጣውን በትዕግሥት መልሶላቸዋል፡፡ ሌላው በፋርስ በስደት ይኖሩ የነበሩ አይሁድ በአስቴር ትእዛዝ የያዙት ሱባዔ ተጠቃሽ ነው፡፡ በዚያን ዘመን አይሁድ በያሉበት እንዲገደሉ አርጤክስስ በማዘዙ ከዚህ የጅምላ ጭፍጨፋ ለመዳን አይሁድ በዐዋጅ ሱባዔ ገብተዋል፡፡ አስቴር ገብታ ንጉሡን ስታናግረው ሌላው ሕዝብ በውጭ ዐዋጅ ዐውጀው ሱባዔ ገብተው ፈጣሪያቸውን ተማጽነዋል (አስቴር ፬፥፲፮-፳፰)፡፡

በአገራችን ኢትዮጵያም ይህን የመሰለ የዐዋጅ ሱባዔ በዐፄ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት ተደርጓል፡፡ ፋሽስት ጣልያን አገራችንን በመውረር ኢትዮጵያን ቅኝ ተገዥ ለማድረግ ድንበሯን አልፎ በመጣበት ወቅት ንጉሠ ነገሥት ምኒልክ ‹‹ጉልበት ያለህ በጉልበትህ፣ ጉልበት የሌለህ በጸሎትህ ርዳኝ›› በማለት የዐዋጅ ሱባዔ መያዛቸው ይነገራል፡፡ በዚህም መሠረት በየገዳማቱ ምሕላ ተይዟል፡፡ ንጉሡም ታቦተ ጊዮርጊስን ይዘው ዓለምን እጅግ ባስደነቀ መልኩ ጥቁሮችን ለነጻነታቸው እንዲነሣሡ የሚያስችል ፋና ወጊ የኾነ ድል አግኝተው አገራችንን ለቅኝ ግዛት ያሰበውን ፋሽስት ጣልያንን ማሸነፋቸው በከፍተኛ ስሜት የምናስታውሰው ታሪክ ነው፡፡

የሱባዔ ቅድመ ዝግጅት

ሱባዔ መግባት የሚፈልግ ምእመን ቅድመ ዝግጅት ማድረግ ይኖርበታል፡፡ ያለምንም ዝግጅት ሱባዔ መግባት ለፈተና ያጋልጣል፡፡ ስለዚህ ቅድመ ሱባዔ (ሱባዔ ከመግባት አስቀድሞ)፣ ጊዜ ሱባዔ (በሱባዔ ጊዜ) እና ድኅረ ሱባዔ (ከሱባዔ በኋላ) ዝግጅት ማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡

ቅድመ ሱባዔ (ሱባዔ ከመግባት አስቀድሞ)

በመጀመሪያ ሱባዔ የምንገባበትን ምክንያት ለይቶ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ አንድ ሰው ሱባዔ የሚገባበትን ዓላማ ለይቶ ካስቀመጠ ከሱባዔ በኋላ የሚጠበቀውን ነገር ማግኘት አለማግኘቱን ይረዳል፡፡ ይህ ሳይኾን ሱባዔ ቢገባ ከሱባዔው በኋላ የጠየቀው ነገር ስለሌለ ድካሙ ዋጋ ያጣል፡፡ ስለዚህ ሱባዔ ከመግባታችን በፊት ለምን ሱባዔ ለመግባት እንዳሰብን ለይተን ማወቅ ይኖርብናል፡፡ ሱባዔ ለመግባት የወሰንበትን ምክንያት ከለየን በኋላ ምክንያታችንን ይዘን የንስሐ አባታችንን ማማከር ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም በምክረ ካህን መጓዝ ክርስቲያናዊ ግዴታ ነውና፡፡ ከዚህም ባሻገር በአባትነታቸውና በሕይወት ልምዳቸው ምን ማድረግ እንደሚገባን ምክር ለማግኘት እገዛ ያደርጉልናል፡፡ ስለኾነም ቅድመ ሱባዔ ከንስሐ አባት ጋር መመካከር ተገቢ ነው፡፡

ለምሳሌ አንድ ሰው በሱባዔ ወቅት ልዩ ልዩ ፈተናዎች ቢያጋጥሙት የተሰጠውን ምክር በመጠቀም ፈተናውን ለመቋቋም ይችላል፡፡ እንደዚሁም የንስሐ አባቱ በሱባዔ ወቅት በጸሎት እንዲያስቡት መማከር ከአንድ ምእመን ይጠበቃል፡፡ ሱባዔ ለመግባት ስናስብ ለምን ያህል ቀናት መቆየት እንዳለብን መወሰን ያስፈልጋል፡፡ ሱባዔ ከዚህ እስከዚህ እቆያለሁ ብለን ዕቅድ የምንይዝበት ነው፡፡ እንደ ዓቅማችንና እንደ ችሎታችን መጠን ከዚህ ቀን እስከዚህ ብለን በመወሰን ሱባዔ መግባት ተገቢ ነው፡፡ ለምሳሌ ምንም ዓይነት ልምድ ሳይኖረው አንድ ሰው በዋሻ እዘጋለሁ ቢል ከጥቅሙ ጉዳቱ ሊያመዝን ይችላል፡፡ ምክንያቱም በሱባዔ ወቅት ፈተና ስለሚበዛ የሚመጣበትን ፈተና መቋቋም ባለመቻሉ ሱባዔውን ሊያቋርጥ ይችላል፡፡ ስለዚህ ቅድመ ሱባዔ ዓቅምንና ችሎታን አገናዝቦ መወሰን ተገቢ ነው፡፡

ሌላው ቅድመ ሱባዔ ለሱባዔ ተስማሚ የኾነ ወቅትና ቦታ መምረጥ ተገቢ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን በአብዛኛው ሱባዔ የሚገባው አጽዋማትን ተከትሎ ነው፡፡ ስለዚህ ሱባዔ የምንገባበት ወቅት የጾም ወቅት መኾን አለመኾኑን መለየት ያስፈልጋል፡፡ በአጽዋማት ወቅት የሚያዝ ሱባዔ ለተሐራሚ ጠቀሜታው እጅግ የጐላ ነው፡፡ ምክንያቱም በአጽዋማት ወቅት ብዙ አባቶች ሱባዔ ስለሚይዙ ከአባቶች ጸሎት ጋር ልመናችንና ጸሎታችን ሊያርግ ይችላል፡፡ ስለዚህ ወቅትን ለይቶ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡

ከዚህ ላይ ከወርኃ አጽዋማት ውጭ ሱባዔ አይያዝም ለማለት አይደለም፡፡ አንድ ሰው ፈተና ከአጋጠመው በማንኛውም ጊዜ ሱባዔ ሊገባ ይችላል፡፡ ከዚህም ባሻገር ሱባዔ የምንይዝበትን ቦታ መምረጥ አለብን፡፡ ለሱባዔ የምንመርጣቸው ቦታዎች ለፈተና የሚያጋልጡ መኾናቸውን ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡ ይኸውም ሱባዔ ከተገባ በኋላ ሕሊናችን እንዳይበተን እገዛ ያደርግልናል፡፡ ጫጫታና ግርግር የሚበዛበት ቦታ በሰቂለ ሕሊና ለመጸለይ አያመችም፡፡ ስለዚህ ሱባዔ የምንይዝባቸው ቦታዎች ከከተማ ራቅ ያሉ ገዳማትና አድባራት ቢኾኑ ተመራጭ ነው፡፡

ጊዜ ሱባዔ (በሱባዔ ጊዜ)

በጸሎት ሰዓት ዓምድና ግድግዳ ሳይደገፉ፣ መቋሚያ ሳይዙ በሁለት እግር ቀጥ ብሎ በመቆም መጸለይ ይኖርብናል፡፡ እንደዚሁም ፊትን ወደ ምሥራቅ መልሶ መቆም ወዲያና ወዲህ፣ ወደ ግራ፣ ወደ ቀኝ አለመዟዟር፤ በሰፊሐ እድ፣ በሰቂለ ሕሊና ኾኖ መጸለይ ይገባል (መዝ. ፭፥፫)፤ መዝ. ፻፴፫፥፪፤ ዮሐ. ፲፩፥፵፩)፡፡ በመጨረሻም ሱባዔ የገባ ሰው ሱባዔውን ሳይጨርስ ወይም ሱባዔውን አቋርጦ ከማንም ሰው ጋር ፈጽሞ መገናኘት የለበትም፡፡

ድኅረ ሱባዔ (ከሱባዔ በኋላ)

ለቀረበ ተማኅጽኖ እግዚአብሔር የሚያደርግልንን ነገር መጠበቅ ይኖርብናል፡፡ እግዚአብሔር ላቀረብንለት ምልጃና ጸሎት እንደ ልባችን መሻት፣ እንደ እርሱ ቸርነት እርሱ በወደደ ጊዜ ያደርግልናል፡፡ ከሱባዔ በኋላ መጀመሪያ የምናገኘው የሕሊና ሰላምን ነው፡፡ ይህም ትልቅ የአምላክ ስጦታ ነው፡፡ ከዚህ ባሻገር ሱባዔ ገብተን ያሰብነውን ካላገኘን ዳግመኛ ተዘጋጅተን እስከ መጨረሻው ሰዓት መጽናትና መማጸን ይኖርብናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡