በዓለ ግዝረት

our-lord

በዝግጅት ክፍሉ

ጥር ፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ክብር ምስጋና ይድረሰውና የጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ግዝረት በየዓመቱ ጥር ፮ ቀን በቤተ ክርስቲያናችን ይከበራል፡፡ ጥር ፮ ቀን በሚነበበው መጽሐፈ ስንክሳር ተጽፎ የሚገኘውን የጌታችንን የግዝረት ታሪክም በሉቃስ ወንጌል አንድምታ ትርጓሜ ከተቀመጠው ትምህርት ጋር በማጣቀስ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

ልሳነ ዕፍረት ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ጌታ ክርስቶስ በሥጋው ግዝረትን ተቀበለ፡፡ ለአባቶች የተሰጠውን ቃል ኪዳን ይፈጽም ዘንድ፤›› በማለት እንደ ተናገረው /ሮሜ.፲፭፥፰/፣ የክብር ባለቤት መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤተ ግዝረት በመግባት የኦሪትን ሕግ ፈጽሟል፡፡ በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈ በስምንተኛው ቀን እንደ ኦሪቱ ሥርዓት ግዝረት ይፈጸምለት ዘንድ ሕፃኑ ጌታችንን ወደ ቤተ መቅደስ ወሰዱት፡፡ ስሙም ገና በሥጋ ሳይፀነስ የእግዚአብሔር መልአክ ባወጣለት ስም ‹‹ኢየሱስ›› ተብሎ ተጠራ /ሉቃ.፪፥፳፩-፳፬/፡፡ መጥምቁ ዮሐንስ ሲገረዝ የሊቀ ካህን ልጅ ነው ብለው ሊገርዙት ወደ እርሱ መጡ፡፡ ጌታችን ግን ወደ ምድር የመጣው ለትሕትና ነው እንጂ ለልዕልና አይደለምና ወሰዱት አለ /ትርጓሜ ወንጌለ ሉቃስ/፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም አረጋዊው ዮሴፍን ‹‹እንደ ሕጉ ልጄን እንዲገርዘውና ስሙንም እንድንሰይመው ብልህ የኾነ ገራዥ ሰው አምጣልኝ፤›› አለችው፡፡ ጻድቁ ዮሴፍም እንዳዘዘችው የሚገርዝ ባለሙያ ይዞ መጣ፡፡ ባለሙያውም በእናቱ በንጽሕት ድንግል ማርያም ክንድ ላይ ሕፃኑ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ባየው ጊዜ ‹‹እንድገርዘው በጥንቃቄ ያዙት›› አላቸው፡፡ ጌታ ኢየሱስም ‹‹ባለሙያ ገራዥ ሆይ! ደሜ ሳይፈስ ልትገርዘኝ ትችላለህን? በዕለተ ዓርብ በመስቀል ስሰቀል ካልኾነ በስተቀር ደሜ አይፈስምና፡፡ ጐኔን በጦር ሲወጉኝ ያን ጊዜ ውኀና ደም ይፈሳል፡፡ ይኸውም ለአዳምና ለሚያምኑ ልጆቹ መድኀኒት ይኾናል፤›› አለው፡፡

የክብር ባለቤት ጌታችን የተናገረውን ይህን ቃል ባለሙያው በሰማ ጊዜም አደነቀ፡፡ ዕቃውንም ሰብስቦ ተነሣና ከጌታችን እግር በታች ወድቆ ሰገደ፡፡ ያንጊዜም ምላጮቹ በእጁ ላይ እንዳሉ እንደ ውኀ ቀለጡ፡፡ ክብርት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምንም ‹‹ከሴቶች ተለይተሽ አንቺ የተባረክሽ ነሽ፡፡ የማኅፀንሽም ፍሬ የተባረከ ነው፡፡ ይህ ልጅሽ ስለ እርሱ ነቢያት ትንቢት የተናገሩለት የሕያው አምላክ ልጅ ነው፤›› አላት፡፡

ጌታችንም ባለሙያውን ‹‹እኔ ነኝ! ትገዝረኛለህን ወይስ ተውክ? ወይስ የአባቶቼ አባቶች እንዳደረጉ ላድርግ?›› አለው፡፡ ባለሙያውም መልሶ ‹‹የአባቶችህ አባቶች እነማን ናቸው?›› ሲል ጠየቀው፡፡ ጌታችንም አብርሃም፣ ይስሐቅ፣ ያዕቆብ የሕዝቡ ዅሉ አባት እንደ ኾኑ ካስገነዘበው በኋላ ‹‹ለእነርሱም ይህ ግዝረት አስቀድሞ ከአባቴ ዘንድ ተሰጣቸው›› በማለት የግዝረትን ሕግ አስረዳው፡፡ ባለሙያውም ይህን ምሥጢር ሲሰማ ‹‹እኔ ከአንተ ጋር እነጋገር ዘንድ አልችልም፡፡ በአንተ ህልውና መንፈስ ቅዱስ አለና፤›› ብሎ የኢየሱስ ክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት መሰከረ፡፡

በዚህ ጊዜ ጌታችን ዐይኖቹን ወደ ሰማይ አቅንቶ ‹‹አባት ሆይ ለአብርሃም፣ ለይስሐቅ፣ ለያዕቆብ አስቀድሞ ግዝረትን የሰጠሃቸው፤ ያቺን ግዝረት ዛሬ ለእኔ ስጠኝ›› አለ፡፡ ያንጊዜም ያለ ሰው እጅ በጌታችን ላይ ግዝረት ተገለጠ (የግዝረት ምልክት ታየ)፡፡ ከዚህ ላይ ጌታችን ወደ አባቱ ወደ እግዚአብሔር አብ ልመና ማድረሱ የለበሰው ሥጋ የአብርሃም፣ የይስሐቅ፣ የያዕቆብ መኾኑንና ጸሎት ማቅረብ የሚስማማው ሥጋን መልበሱን ለማጠየቅ ነው እንጂ በእርሱና በአብ መካከል ልዩነት ኖሮ አይደለም፡፡

ጌታችን ድንግልናዋን ሳያጠፋ ከድንግል ማኅፀን እንደ መውጣቱ ግዝረቱም አይመረመርም፡፡ በተዘጋ ቤት ወደ ሐዋርያት እንደ ገባና እንደ ወጣ ዅሉ እርሱ በሚያውቀው ረቂቅ ጥበብ ከሥጋው ምንም ምን ሳይቈረጥ፣ ምንም ደም ሳይፈሰው መገረዙ ተገለጠ፡፡

ገራዡም የጌታችንን ቃል ከመስማቱ ባሻገር በሥጋው ላይ የተደረገውን ተአምር ባየ ጊዜ እጅግ አደነቀ፡፡ ከክብር ባለቤት ከጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እግር በታች ወድቆም ሦስት ጊዜ ሰገደና ‹‹በእውነት አንተ የእግዚአብሔር ልጅ፣ የእስራኤልም ንጉሥ ነህ!›› በማለት በክርስቶስ አምላክነት አመነ፡፡ ከዚህ በኋላ ያየውንና የሰማውን ዅሉ እየመሰከረ ወደ ቦታው ተመለሰ፡፡ የእግዚአብሔር አብ ጸጋ፣ የእግዚአብሔር ወልድ ፍቅር፣ የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስም ኅብረት በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት ያለ ጥርጥር በፍጹም ልባችን ከምናምን ምእመናን ጋር ይኹን! /፪ኛቆሮ.፲፫፥፲፬/፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ሥጋዌ – የድኅነት ቍልፍ – የመጨረሻ ክፍል

በመምህር ፀሐዬ ዳዲማስ

ታኅሣሥ ፳፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ቅዱስ ያሬድ ቅዱሳን መላእክት በምስጋናቸው የተናገሩለትን ሰላም ያስተማረውና የተረጐመው ከድኅነት ጋር አያይዞ ነው። የመላእክቱን አዲስ ምስጋና በተረጐመበት አንቀጸ ብርሃን በተባለው የድርሰቱ ክፍልም፡- ‹‹ወዓዲ ርእዩኪ በውስተ በዓት ለኪ ለባሕቲትኪ ምስለ ሕፃንኪ ወይቤሉ ሰላም በዲበ ምድር ወሶበ ርእዩ እንዘ ይለብስ ሥጋ ዚአነ ዘነሥአ እምኔኪ ሰገዱ እንዘ ይብሉ ለእጓለ እመሕያው ሠምሮ፤ እንደ ገናም ከሕፃኑ ልጅሽ ጋር አንቺን ብቻሽን በበረት ውስጥ ባዩሽ ጊዜ ‹በምድር ላይ ሰላም [ኾነ]› አሉ፤ ከአንቺ የነሣውን የእኛን ሥጋ ተዋሕዶ ባዩት ጊዜም ‹የሰውን ልጅ ወደደው› እያሉ ሰገዱ፤›› ሲል ተናግሮአል (መጽሐፈ ምዕራፍ፣ አንቀጸ ብርሃን፣ ገጽ ፻፳፯)። በዚህ ድርሰቱም የመላእክቱን ምስጋና፣ የሰው ልጆችን ድኅነት እንድንረዳ ቅዱስ ያሬድ በጥልቀት አስተምሮናል።

ቅዱስ ያሬድ ስለ ሰላም ሲነግረን ስለ ድኅነት እየመሰከረ እንደ ኾነ እና ከልደተ ክርስቶስ ጋር ያለውን ግንኙነት እያስረዳን መኾኑን መገንዘብ ያስፈልጋል። ይህን የቅዱሳንን ልቡና ለመረዳት መጽሐፍ ቅዱስን በማንበብና ሊቃውንትን በመጠየቅ የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮን ማገናዘብ እጅግ ጠቃሚ ነው። ቅዱስ ጳውሎስ የኤፌሶን ሰዎችን፡- ‹‹አሁን ግን እናንተ በፊት ርቃችሁ የነበራችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ ኾናችሁ በክርስቶስ ደም ቀርባችኋል። እርሱ ሰላማችን ነውና፤ ሁለቱን ያዋሐደ በአዋጅ የተነገሩትንም የትእዛዛትን ሕግ ሽሮ በመካከል ያለውን የጥል ግድግዳን በሥጋው ያፈረሰ፤ ይህም ከሁለታቸው አንድን አዲስን ሰው በራሱ ይፈጥር ዘንድ ሰላምንም ያደርግ ዘንድ፤›› በማለት በክርስቶስ የተገኘውን ሰላም አስተምሯቸዋል (ኤፌ. ፪፥፲፫-፲፭)፡፡ በዚህም የሐዋርያው መልእክት ክርስቶስ የሰጠንም ድኅነት ሰላም እንደተባለ እናስተውላለን።

የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐርበኛ ሐዋርያዊው ቅዱስ አትናቴዎስም፡- በማቴዎስ ወንጌል ፲፩፥፳፰ ላይ በሚገኘው ‹‹ወደ እኔ ኑ፤››  እና በሉቃስ ወንጌል ፲፥፳፪ ላይ በተጻፈው፡- ‹‹ዅሉ ከአባቴ ዘንድ ተሰጥቶኛል›› በሚሉት ጌታችን ባስተማራቸው የወንጌል ቃላት ላይ ተመሥርቶ ባቀረበው ትምህርት የድኅነትን ሰላምነት እንዲህ በማለት ያስረግጥልናል፤ ‹‹አስቀድሞ ሰው አልነበረምና በኋለኛው ዘመን ግን ሰውን ያድን ዘንድ ሰው ኾነ። በመጀመርያው ቃል ሥጋ አልነበረም፤ ከዘመናት በኋላ ሥጋ ኾነ እንጂ፡፡ ሐዋርያት እንደ ነገሩን ከእርሱ ጋር የነበረብንን ጠላትነት ያስታረቀልን፣ በእኛ ላይ ተቀምጠው የነበሩትን ትእዛዛት ያጠፋልን በዚህ ሥጋ ነው፡፡ ይህን በማድረጉም ሁለቱን አንድ አዲስ ሰው ያደርግ ዘንድ፣ ሰላምን ያሰፍን ዘንድ፣ ሁለቱንም አንድ አድርጎ ከአብ ጋር ያስታርቅ ዘንድ ነው፤›› (NPNF V2-04፣ ገጽ 300-301)።

ስለ ኾነም ቅዱስ ያሬድ በክርስቶስ ልደት የተቀበልነውን ሰላም እንድንከተል፣ በክርስቶስ ሥጋ መልበስ ያገኘነውን ድኅነት ገንዘብ እንድናደርግ በምስጋናው ዅሉ ይመክረናል፡፡ ዘማሪው በተጨማሪም ክርስቶስ ይህን ሰላም የሰጠን በደላችንን ይቅር ብሎ፣ … ከኃጢአት በስተቀር ሰው የሚኾነውን ኾኖ እንደ ኾነ በማስረገጥ፤ እንደዚሁም እግዚአብሔር ሰው ኾኖ ሰውን ለማዳን ያበቃው ይቅር ባይ ባሕርዩ እንደ ኾነ እንድናምን ያስረዳናል። በሌላኛው የምስጋና ድርሰቱም ‹‹ብርሃን መጽአ ኀቤነ ከመ ያርኢ ምሕረቶ በላዕሌነ ውእቱ ኢየሱስ ክርስቶስ … ርእዩ ዘከመ አፍቀረነ እግዚአብሔር፤ በእኛ ላይ ምሕረቱን ያሳይ ዘንድ ብርሃን ወደ እኛ መጣ፤ እርሱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ እግዚአብሔር ምንኛ እንደ ወደደን ተመልከቱ፤›› በማለት ሊቁ ዘምሯል (ድጓ ዘዘመነ ልደት)፡፡ ይህም እግዚአብሔር ሰዎችን እንዲያድን ያደረገው ለሰው ልጆች ያለው ልዩ ፍቅር እንደ ኾነ የሚያስገነዝበን ድንቅ ትምህርት ነው። በሊቁ ትምህርት መሠረት የሰው ልጆችን ለድኅነት ካበቁት የእግዚአብሔር ባሕርያት መካከል ይቅር ባይነት እና ፍቅር ዋና ዋነኛዎቹ እንደ ኾኑ ለመረዳት እንችላለን፡፡

በአጠቃላይ የሰዎችን ሥጋ ተዋሕዶ ሰዎችን እንዲያድን የፈቀደ ራሱ እግዚአብሔር አምላካችን ነው። ይህ ደግሞ አምነን የምንቀበለውና በተወደደው የድኅነት መንገድ ለመጓዝ መንገዳችንን የሚያቀናልን እንጂ መርምረን የምንደርስበት ምሥጢር አይደለም። ይልቁንም እኛ ድነን ለዘመናት አጥተናት ወደ ነበረችው ገነት እንድንመለስ እና በራሳችን ስሕተት በእኛና በእግዚአብሔር መካከል ተፈጥሮ የነበረው የጥል ግድግዳ ፈርሶ ከእግዚአብሔር ጋር እንድንኖር የእግዚአብሔር ሰው መኾን (ሥጋዌ) እጅግ አስፈላጊ እንደ ነበረ፣ እግዚአብሔር ሰው ኾኖ ሰውን እንዲያድን ካገበሩት ባሕርያቱ መካከልም ይቅር ባይነቱ (መሐሪነቱ) እና ፍቅሩ መኾናቸውን እያሰብን ከቅዱስ ያሬድ ጋር ‹‹አናኅስዮ አበሳነ አፍቂሮ ኪያነ ፈነወ ለነ ወልዶ መድኅነ፤ በደላችንን ይቅር ብሎ እኛን ወዶ አዳኝ ልጁን ወደኛ ሰደደልን፤›› እያልን በማመስገን የመድኃኒታችንን በዐለ ልደት በደስታ እናከብራለን።

በዐሉን ስናከብርም እንደ መላእክቱ እና እንደ ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት አዲስ ምስጋናን ለእግዚአብሔር በመቀኘት እንጂ ከእግዚአብሔር በሚለዩን በዓለም ዳንኪራዎች እንዳይኾን ራሳችንን መግዛት ይኖርበታል፡፡ ሥጋችንን ተዋሕዶ ለድኅነት የተገለጠልንን መድኃኒታችንን እያሰብን ድኅነታችንን ገንዘብ በምናደርግበት በታላቁ በዓላችን ወቅት ዘመን በወለዳቸው ኃጢአቶች ድኅነታችንን እንዳናጣ ከመጠንቀቅ ጋርም በዓሉን የበረከት በዓል ልናደርገው እንደሚገባን አንርሳ፡፡ አምላካችን ከጥልቅ ፍቅሩ የተነሣ ለድኅነታችን የተገለጠውን መድኅን የምንዘክርበትን በዓላችንን ዓለም ዅሉ ወደ ድኅነት የሚቀርብበት በዓል ያድርግልን፡፡

በማይጠቀለል ሦስትነት፣ በማይከፋፈል አንድነት ጸንቶ የኖረ እና የሚኖር፤ አስቀድሞ በአርአያውና በአምሳሉ የፈጠረውን ሥጋ በመዋሐድ ለሰው ልጆች ያለውን የማይለካና በቃላት ሊገለጥ የማይችል ፍቅር ያሳየ፤ በእያንዳንዷ ቅጽበት ከቸርነቱ ብዛት፣ ከጸጋው ምልአት የተነሣ ፍጥረታትን የሚመግብ፤ ልሳናት ዅሉ የሚያመሰግኑት፤ ጕለበቶች ዅሉ የሚንበረከኩለት ልዑል እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይድረሰው! ተወልዶ እንዲያድነን አንድያ ልጁን ለላከልን ለእግዚአብሔር አብ፤ ከአባቱ ዕቅፍ ሳይለይ ሥጋችን ተዋሕዶ ላዳነን ለእግዚአብሔር ወልድ፤ በዅሉም የሚኖር፣ ዅሉንም ለሚያከናውን ለእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ክብር፣ ምስጋና ይዅን፤ አሜን፡፡

ማስገንዘቢያ፡-

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! ይህ ትምህርት ከታኅሣሥ ፲፮ – ፴ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በወጣው ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ በዓውደ ሃይማኖት ዓምድ ሥር ‹‹አዳኝ ልጁን ወደ እኛ ሰደደልን›› በሚል ርእስ ለንባብ መብቃቱን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡

በሐዊረ ሕይወቱ መደሰታቸውን ተሳታፊዎች ተናገሩ

በዝግጅት ክፍሉ

ታኅሣሥ ፳፯ ቀን ፳፻፱ .

img_0298

ዓለም ገና ደብረ ናዝሬት ኢየሱስ ክርስቶስ እና ቅድስት ማርያም ገዳም

img_0351

፲፩ኛው የማኅበረ ቅዱሳን ሐዊረ ሕይወት በዓለም ገና ደብረ ናዝሬት ኢየሱስ ክርስቶስ እና ቅድስት ድንግል ማርያም ገዳም ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ መምህራነ ቤተ ክርስቲያን፣ አባቶች ካህናትና ዐሥራ አንድ ሺሕ የሚኾኑ ምእመናን በተገኙበት ታኅሣሥ ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም መካሔዱ የሚታወስ ነው፡፡

img_0325

በሐዊረ ሕይወቱ ጠዋትና ከሰዓት በኋላ በተከናወነው መርሐ ግብር በብፁዕ አቡነ ሉቃስ፤ በማኅበሩ ሰባክያነ ወንጌል መ/ር ምትኩ አበራና መ/ር ያረጋል አበጋዝ ልቡናን የሚገዛና ድካመ ነፍስን የሚጠግን ሰፊ ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል፡፡

img_0296

ምክረ አበው አቅራቢ አባቶች

ከዚሁ ዅሉ ጋርም ለ ‹‹ምክረ አበው›› በተጋበዙት በቆሞስ አባ ሳሙኤል በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የብሉያትና ሐዲሳት ትርጓሜ መምህር፤ በአባ ገብረ ኪዳን በደቡብ ጎንደር እስቴ መካነ ኢየሱስ ደብር የአባ ኤስድሮስ ጉባኤ ቤት የሐዲሳት ትርጓሜ መምህርና የብሉያት ደቀ መዝሙር፤ በመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ በአዲስ አበባ የምሥራቀ ፀሐይ ቀበና መድኀኔ ዓለም ደብር የሐዲሳት ትርጓሜ መምህር እና የስብከተ ወንጌል ክፍል ሓላፊ የብዙ ምእመናንን ጥያቄ የሚመልስ ትምህርት ቀርቧል፡፡

img_0333

የማኅበሩ መዘምራን ወረብና መዝሙር ሲያቀርቡ

በማኅበሩ ዘማርያንና በሊቀ መዘምራን ዲ/ን ቴዎድሮስ ዮሴፍ የቀረበው ያሬዳዊ ወረብና መዝሙርም የጉባኤው ክፍል ነበር፡፡

የሐዊረ ሕይወቱ ዐቢይ ኰሚቴ ሰብሳቢ አቶ ኤርምያስ ዓለሙ ለዝግጅት ክፍላችን እንዳስታወቁት ትኬት በመግዛት የመጡ ስምንት ሺሕ፤ ለልዩ ልዩ አገልግሎት ለመስጠት የተመደቡ አንድ ሺሕ፤ ከዓለም ገና እና ከአካባቢው የመጡ ደግሞ በግምት ሁለት ሺሕ፤ በድምሩ ዐሥራ አንድ ሺሕ የሚኾኑ ምእመናን በመርሐ ግብሩ ላይ የታደሙ ሲኾን በሐዊረ ሕይወቱ መደሰታቸውንም ተሳታፊዎች ተናግረዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው ቃለ ምዕዳን በሰጡበት ወቅት ‹‹ይህ ጉባኤ በዚህ ቦታ መዘጋጀቱ ለገዳሙ ብቻ ሳይኾን አጠቃላይ ለሀገረ ስብከታችን ትልቅ ዕድል ነው፤ በዚህ አካባቢ የሚገኙ ምእመናንም በመርሐ ግብሩ ትልቅ ተስፋ አግኝተዋል፤›› ካሉ በኋላ ‹‹ይህንን ጉባኤ በዚህ ቦታ በማካሔድ ሕዝበ ክርስቲያኑን በማስደሰቱ ማኅበሩን አመስግነዋለሁ፤›› በማለት የማኅበሩን አገልግሎት አበረታተዋል፡፡

ብ

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ እና ብፁዕ አቡነ ሉቃስ ከከፊል የጉባኤው ተሳታፊዎች ጋር

ከመርሐ ግብሩ ተሳታፊዎች መካከል አንዳንዶቹ በሐዊረ ሕይወቱ በመሳተፋቸው በርካታ መንፈሳዊ ቁም ነገር ማግኘታቸውን፣ በትምህርቱ ነፍሳቸው መርካቷንና አእምሯቸውም መደሰቱን ጠቅሰው ይህን ዅሉ ምእመን በአንድ ድንኳን ሥር አሰባስቦ፤ ቍርስ እና ምሳ መግቦ ቃለ እግዚአብሔር እንዲማር በማድረጉ ማኅበረ ቅዱሳንን አድንቀዋል፡፡ አያይዘውም ‹‹መርሐ ግብሩ ከዓመት ሁለት ጊዜ ብቻ ሳይኾን በየወሩ ቢካሔድልን?›› የሚል አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

ed

የጉባኤው ተሳታፊ አባቶችና ወንድሞች በከፊል

የዓለም ገና እና የአካባቢው ማኅበረ ካህናትና ምእመናንም ሐዊረ ሕይወቱ በአካባቢያቸው በመካሔዱ ካገኙት መንፈሳዊ ትምህርት ባሻገር ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን የጠበቀ መንፈሳዊ ጉባኤ የማዘጋጀት ልምድን ከማኅበረ ቅዱሳን መማራቸውንም ተናግረዋል፡፡

በዕለቱ በማኅበሩ ሰብሳቢ በአቶ ታምሩ ለጋ የማኅበሩ መልእክት የቀረበ ሲኾን በመልእክቱም ማኅበሩ በሚያበረክተው የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በመሳተፍ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በጋራ ለመደገፍና አገልግሎቷን በሚፈለገው ደረጃ ለማሳደግ መላው ሕዝበ ክርስቲያን የበኩሉን እገዛ ያደርግ ዘንድ ሰብሳቢው ጥሪያቸውን በቤተ ክርስቲያን ስም አስተላልፈዋል፡፡

wo

የጉባኤው ተሳታፊ እናቶችና እኅቶች በከፊል

እንደዚሁም የማኅበሩ የስድስት ዓመት ስልታዊ ዕቅድ የትኩረት አቅጣጫዎችን የስልታዊ ዕቅዱ ክንውንና ትግበራ ጽ/ቤት ሓላፊ አቶ ፋንታኹን ዋቄ አቅርበው ለዕቅዱ መሳካትም ምእመናን በሚቻላቸው ዓቅም ዅሉ የድርሻቸውን አስተዋፅዖ እንዲያበርክቱ አሳስበዋል፡፡

በመቀጠልም ሐዊረ ሕይወቱ በተሳካ ኹኔታ እንዲከናወን ድጋፍና ትብብር ያደረጉ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስንና የሀገረ ስብከቱ ሠራተኞችን፤ የሰበታ አዋስ ወረዳ ቤተ ክህነትና ወረዳ ማእከሉን፤ የደብረ ናዝሬት ኢየሱስ ክርስቶስና ቅድስት ማርያም ገዳም ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤትን፣ ማኅበረ ካናትንና ምእመናንን፤ ከፌዴራል መንግሥት ጀምሮ በየደረጃው እስከ ከተማ አስተዳደሩ ድረስ የሚገኙ የመንግሥት አካላትን ማኅበሩ በእግዚአብሔር ስም አመስግኗል፡፡

11

መርሐ ግብሩ በጸሎት ሲፈጸም

በመጨረሻም ፲፩ኛው የማኅበረ ቅዱሳን ሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ ተፈጽሟል፡፡

ሥጋዌ – የድኅነት ቍልፍ – ክፍል ሁለት

በመምህር ፀሐዬ ዳዲማስ

ታኅሣሥ ፳፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በስድስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን በምስጋናው ብርሃን ያበራው ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድም ነገረ ሥጋዌ ከሰው ልጆች ድኅነት ጋር ያለውን ቍርኝነት ጥልቅ ምሥጢር ባለው በመጽሐፈ ድጓ ድርሰቱ ጽፎልን እናነበዋለን። ቅዱስ ያሬድ በምስጋናው አንሥቶ ከማይጠግባቸው ምስጋናዎች መካከል የአምላክ ሥጋዌ (ሰው መኾን) እና ነገረ ስቅለት ቀዳሚዎች ሲኾኑ የሚያነሣቸውም ከነገረ ድኅነት ጋር በተያያዘ ምሥጢር ነው፡፡ የእግዚአብሔር ሰዎችን የማዳን ተግባራት ከሚመለከቱ ድርሰቶቹ መካከል ለአብነት የሚከተለውን ትምህርት መጥቀስ እንችላለን፤

‹‹ዘዲበ ኪሩቤል ይነብር ወበአርያም ይሴባሕ እምሰማያት እምልዑላን ወረደ አምላክ ያድኅን ዓለመ መጽአ ይክሥት ብርሃነ ይናዝዝ ኅዙናነ ወልድ ተወልደ ለነ ወሠርዐ ሰንበተ ለሰብእ ዕረፍተ ውእቱኬ ወልደ አምላክ ውእቱ ወልድ ዋሕድ ውእቱ፤ በኪሩቤል ላይ የሚኖር በአርያምም የሚመሰገን ከሰማያት ከልዑላን ወረደ፤ አምላክ ዓለምን ያድን ዘንድ መጣ፤ ብርሃንን ይገልጥ ዘንድ፣ ያዘኑትን ያጽናና ዘንድ፣ [እግዚአብሔር] ወልድ ተወለደልን፡፡ ለሰዎች ዕረፍትም ሰንበትን ሠራ፤ እሱም የአምላክ ልጅ ነው፡፡ [እሱም] በተዋሕዶ የከበረ [እግዚአብሔር] ወልድ ነው፤›› (ድጓ ዘዘመነ ልደት)፡፡

እነዚህ የቅዱስ ያሬድ የምስጋና ቃላት እግዚአብሔር ወልድ የሰውን ሥጋ ለብሶ ሰው መኾኑን ከማስረዳታቸውም ባሻገር እግዚአብሔር አምላካችን ሰው በመኾኑ የሰው ልጆች ያገኙትን ጥቅምም የሚያስረግጡ ናቸው። ዘማሪው አምላክ ወልደ አምላክ ዓለምን ያድን፣ ብርሃንን ይገልጥ፣ ያዘኑትንም ያጽናና ዘንድ ከሰማያት እንደ ወረደ እና ወደ ዓለም ወይም ወደ ሰዎች እንደ መጣ ሲነግረን የተለያዩ ጽጌያትን እንደሚቀስም ንብ መጽሐፍ ቅዱስን በማጣቀስ እንደ ኾነ ስንረዳም የአበው ሊቃውንት መጽሐፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮን ልብ እንድንል ያስችለናል።

እግዚአብሔር አብ አንድያ ልጁን እግዚአብሔር ወልድን ወደ ዓለም የላከው ዓለም በልጁ እንዲድን እንደ ኾነ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለኒቆዲሞስ ያስተማረውን ትምህርት ቅዱስ ዮሐንስ በወንጌሉ ጽፎልናል (ዮሐ. ፫፥፲፮)። የነቢያት ትንቢት በክርስቶስ መፈጸሙን ደጋግሞ በማውሳት የሚታወቀው ሐዋርያው እና ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስም የነቢዩ የኢሳይያስ ትንቢት በሥግው ቃል በክርስቶስ እንደ ተፈጸመ በሚያስረዳ የወንጌሉ ክፍል ‹‹‹በጨለማ የተቀመጠው ሕዝብ ታላቅ ብርሃን አየ፤ በሞት አገርና ጥላ ለተቀመጡትም ብርሃን ወጣላቸው› የተባለው ይፈጸም ዘንድ ይህ ኾነ›› በማለት ጽፏል (ማቴ. ፬፥፲፬-፲፮ ኢሳ. ፱፥፪)።

ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስም በተመሳሳይ መልኩ የነቢዩን የኢሳይያስን ትንቢት ጠቅሶ ክርስቶስ በዘመነ ስብከቱ ስለ ራሱ እና ሰው ስለ ኾነበት ምክንያት ሲያስረዳ የተናገረውን ‹‹የነቢዩንም የኢሳይያስን መጽሐፍ ሰጡት፤ መጽሐፉንም በተረተረ ጊዜ ‹የጌታ መንፈስ በእኔ ላይ ነው፤ ለድሆች ወንጌልን እሰብክ ዘንድ ቀብቶኛልና፤ ለታሰሩትም መፈታትን፣ ለዕውሮችም ማየትን እሰብክ ዘንድ፤ የተጠቁትንም ነጻ አወጣ ዘንድ፤ የተወደደችውንም የጌታን ዓመት እሰብክ ዘንድ ልኮኛል› ተብሎ የተጻፈበትን ስፍራ አገኘ። መጽሐፉንም ጠቅልሎ ለአገልጋዩ ሰጠውና ተቀመጠ፤ በምኵራብም የነበሩት ዅሉ ትኵር ብለው ይመለከቱት ነበር። እርሱም ‹ዛሬ ይህ መጽሐፍ በጆሮአችሁ ተፈጸመ› ይላቸው ጀመር፤›› (ሉቃ. ፬፥፲፯-፳፩) በማለት ትንቢቱ መፈጸሙን ተናግሯል።

የነቢዩን ቃላት በምልአት ስንመለከታቸው ‹‹የጌታ የእግዚአብሔር መንፈስ በእኔ ላይ ነው፤ ለድሆች የምሥራችን እሰብክ ዘንድ እግዚአብሔር ቀብቶኛልና፤ ልባቸው የተሰበረውን እጠግን ዘንድ፤ ለተማረኩትም ነፃነትን፣ ለታሰሩትም መፈታትን እናገር ዘንድ ልኮኛል። የተወደደችውን የእግዚአብሔርን ዓመት፣ አምላካችንም የሚበቀልበትን ቀን እናገር ዘንድ፤ የሚያለቅሱትንም ዅሉ አጽናና ዘንድ፤ እግዚአብሔር ለክብሩ የተከላቸው የጽድቅ ዛፎች እንዲባሉ ለጽዮን አልቃሾች አደርግላቸው ዘንድ፤ በአመድ ፋንታ አክሊልን፣ በልቅሶም ፋንታ የደስታ ዘይትን፤በኀዘን መንፈስ ፋንታም የምስጋና መጐናጸፊያን እሰጣቸው ዘንድ ልኮኛል፤›› የሚሉ ናቸው (ኢሳ. ፷፩፥፩)።

እነዚህን አጠቃልሎ ቅዱስ ያሬድ ድኅነተ ሰብእን ሲያመለክት ‹‹ዓለምን ያድን ዘንድ መጣ፡፡ብርሃንን ይገልጥ ዘንድ፤ ያዘኑትን ያጽናና ዘንድ፤ [እግዚአብሔር] ወልድ ተወለደልን፤›› በማለት በዝማሬ አመሰገነ። እግዚአብሔር የሰውን ሥጋ ለብሶ ሰውን ያድን ዘንድ ያስገደደው የገዛ ባሕርዩ ነው፡፡ እግዚአብሔር ሰውን ለማዳን ወደ ዓለም የመጣበትን ምክንያት ብዙ ሊቃውንት በብዙ መንገድ ጽፈዋል። አንዳንዶቹም የማይረገጠውን ረግጠው በድፍረት ‹‹መጽአ በኵርሕ፣ ተገዶ መጣ›› ብለው እስከ ማስተማር በመድረሳቸው ከቤተ ክርስቲያን አንድነት ተለይተዋል። ፍጹማን የኾኑት የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ግን እግዚአብሔር የሰው ልጆችን እንዲያድን ያደረገው ባሕርዩ እንደ ኾነ በምስጋና ድርሰቶቻቸው ጽፈውልናል።

ቅዱስ ያሬድ በበዐለ ኖላዊ ሳምንት በሚደርሰው የድጓ ድርሰቱ ‹‹አናኅስዮ አበሳነ አፍቂሮ ኪያነ ፈነወ ለነ ወልዶ መድኅነ፣ በደላችንን ይቅር ብሎ እኛን ወዶ አዳኝ ልጁን ወደኛ ሰደደልን፤›› በማለት ክርስቶስ ወደ ዓለም የመጣው እኛን ለማዳን መኾኑን ነግሮናል። ሊቁ በዚህ ድርሰቱ እግዚአብሔር አብ እግዚአብሔር ወልድን ለድኅነት ወደ እኛ ወደ ሰዎች የላከልን በይቅር ባይ እና ፍቅርን መሠረት ባደረገው ባሕርዩ እንደ ኾነ ያስረዳል። እጅግ ጥልቅ በኾነ ምሥጢር ነገረ ድኅነትን የሚገልጠውን ሌላኛውን የቅዱስ ያሬድን ምስጋና እናንሣ፤ ‹‹ይእዜኒ ንትልዋ ለሰላም እስመ ተወልደ ክርስቶስ ዮም በሀገረ ዳዊት አናኅስዮ አበሳነ ወልዱ ለአብ ቀዳሜ በኵሩ ኃይሉ ለአብ መጽአ ኀቤነ ይክሥት ብርሃነ ተመሲሎ ኪያነ ሰብአ ዘይከውን ኵሎ ኮነ ዘእንበለ ኃጢአት ባሕቲታ፤›› (ድጓ ዘዘመነ ልደት)፡፡ ትርጕሙም፡- ‹‹እንግዲህማ ሰላምን እንከተላት፤ ዛሬ ክርስቶስ በዳዊት አገር ተወልዷልና፡፡ በደላችንን ይቅር ብሎ የአብ አንድያ ልጁ፣ የአብ ኃይሉ፣ ወደ እኛ መጣ፤ ብርሃንን ይገልጥ ዘንድ፣ እንደ እኛ ሰው ኾነ፡፡ ከብቻዋ ከኃጢአት በቀር ሰው የሚኾነውን ዅሉ ኾነ፤›› ማለት ነው፡፡

ከዚህ የምስጋና ክፍል እንደምንረዳው የጌታችን ልደት የሰላም ምንጭ መኾኑን ነው። ይህ ሰላም ደግሞ ዓለም የምትሰጠው ሰላም አይደለም፤ ድኅነተ ሰብእን የሚያሳይ ሰላም፤ ሰዎች ከእግዚአብሔር ጋር የነበራቸው ልዩነት ተወግዶ ዕርቅ መመሥረቱን የሚያሳይ ሰላም ነው እንጂ። በክርስቶስ ልደት ለዓለም የተሰጠው ሰላም ደግሞ የሚሠራው ሰዎች ዅሉ ሲሹትና ሲከተሉት ነውና ‹‹ንትልዋ ለሰላም›› እያለ በረጅሙ ይሰብካል። ለዚህም ነው መላእክቱ ከእረኞቹ መካከል ተገኝተው፣ ከሰዎች ጋር በአንድነት ኾነው በአዲስ ምስጋና ሲያመሰግኑ ‹‹ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይኹን! ሰላምም በምድር፤ ለሰውም በጎ ፈቃድ፤›› በማለት የዘመሩት (ሉቃ. ፪፥፲፬)።

ይቆየን

ሥጋዌ – የድኅነት ቍልፍ – ክፍል አንድ

በመምህር ፀሐዬ ዳዲማስ

ታኅሣሥ ፳፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጌታችን የሰው ልጆችን የሚያድንበት የማስተማር ሥራው (ወንጌልን መስጠቱን) ሲጀምርም ሲፈጽምም በነገረ ድኅነት ትምህርት ነው። የስብከቱ መነሻ የትምህርተ ድኅነት መዳረሻ የኾነው የመንግሥተ ሰማያትን ነገር ማውሳት ነበር፡፡ ‹‹መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሓ ግቡ እያለ ይሰብክ ጀመር፤›› እንዲል (ማቴ. ፬፥፲፯)። ከሰማያት የወረደበትንና ሰው የኾነበትን የድኅነት ሥራውን ፈጽሞ በትንሣኤው የሰው ልጆችን ሕያውነት አረጋግጦና የዘለዓለምን ሕይወት አውጆ ወደ አባቱ ያረገው ‹‹ወደ ዓለም ዅሉ ሒዱ፤ ወንጌልንም ለፍጥረት ዅሉ ስበኩ። ያመነ የተጠመቀም ይድናል፤ ያላመነ ግን ይፈረድበታል፤›› በማለት ትምህርተ ድኅነታዊ ትእዛዝን ለሐዋርያት በመስጠት ነበር (ማር. ፲፯፥፲፭-፲፮)።

ቅዱስ ጳውሎስም ትምህርተ ክርስትና ከድኅነት ጋር ያለውን የጠበቀ ቍርኝት፣ የማይነጣጠል አንድነት የሚያመለክቱ ኃይለ ቃላትን በመልእክታቱ አስፍሮ ይገኛል። ‹‹የሰበክሁላችሁን ደግሞም የተቀበላችሁትን በእርሱም ደግሞ የቆማችሁበትን በእርሱም ደግሞ የምትድኑበትን ወንጌል አሳስባችኋለሁ›› (፩ቆሮ. ፲፭፥፩) በማለት የቆሮንቶስ ክርስቲያኖችን ሲያሳስብ፣ ‹‹የእውነትን ቃል፣ ይኸውም የመዳናችሁን ወንጌል፤ ሰምታችሁ ደግሞም በክርስቶስ አምናችሁ፣ በተስፋው መንፈስ በመንፈስ ቅዱስ ታተማችሁ›› (ኤፌ. ፩፥፲፫) በማለት ደግሞ ለጊዜው ኤፌሶናውያንን፤ ለፍጻሜው ዳግም የሰው ልጅን ዅሉ ድኅነት መክሯል፡፡ ወንጌላዊው ማርቆስም ስለ አጠቃላይ የክርስትና ትምህርት ምንነት ሲያስረዳ ‹‹ለዘለዓለም ድኅነት የኾነውን የማይለወጠውን ቅዱስ ወንጌል›› በማለት ነው የሚገልጠው (ማር. ፲፮፥፰)።

የክርስትና ትምህርት የድኅነት ትምህርት ነው። ከጅምሩ እስከ ፍጻሜው የሰው ልጆችን መዳን ቁልፍ መጠቅለያውና ማጠንጠኛው ነው። አቀራረቡም ‹‹ነገረ ድኅነታዊ›› ነው – የክርስትና ትምህርት። ከጥንት ጀምሮ ሐዋርያትና ሊቃውንት የወንጌላውያኑን እና የሐዋርያትን አሰረ ፍኖት በመከተል የክርስትናን ትምህርት የጠበቁት ነገረ ድኅነትን አምልቶና አስፍቶ በማስተማር ነው።

ኢትዮጵያውያን ሊቃውንትም እንደዚሁ ትምህርታቸውንና ዝማሬአቸውን ዅሉ ነገረ ድኅነታዊ በማድረግ የክርስቶስ ተከታይነታቸውን፣ የሐዋርያትና የሊቃውንት ልጅነታቸውን አስመስክረዋል። በዚህ አጭር ጽሑፍም ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት የጌታችንን ልደት አስመልክተው ያቀረቡአቸውን የነገረ ድኅነት ትምህርቶች በአጭሩ እናቀርባለን፡፡

በክርስትና ትምህርት ከመጀመርያዎቹ የክርስትና ዘመናት ጀምሮ የሊቃውንትን ከፍተኛ ትኩረት የሳበው የእግዚአብሔር ሰው መኾን ነው። ሰው ሊድን የሚችለው በእግዚአብሔር ነው፣ እግዚአብሔር ደግሞ  የወደቀውን ሰው ለማዳን የወደደው ራሱ የሰዎችን ሙሉ (ፍጹም) ማንነት፣ ከኃጢአት በቀር፣ ወስዶ (ተዋሕዶ) ነው። ስለዚህ የድኅነት መነሻ ቍልፉ የእግዚአብሔር ፍጹም ሰው መኾን ነው። ቅዱስ አግናጥዮስ ምጥው ለአንበሳ ‹‹እግዚአብሔር ለሰዎች ሰው እንደ ኾነ መሰላቸው እንጂ እሱ ሰው ሊኾን አይችልም›› በማለት ለሚያስተምሩት ለዶሰቲስቶች (Docetists) መቃወምያ አድርጎ ባቀረበው እና ለትራልዮን ሰዎች በጻፈው መልእክቱ የሚከተለውን ጽሑፍ አበርክቶልናል፤

‹‹ከእግዚአብሔር የራቁ እምነት የሌላቸው ሰዎች ‹ሰውን መሰለ እንጂ የሰውን ፍጹም ሥጋ ለራሱ አልወሰደም (አልለበሰም)፣ የሞተውም በምስል ነው እንጂ እሱ በትክክል መከራ አልተቀበለም› እንደሚሉት ከኾነ [እጄንና እግሬን] ለምን [በሰንሰለት] እታሰራለሁ ይመስላችኋል? ለምንስ ለተራቡ አናብስት ለመሰጠት ይናፍቀኛል?… ድንግል ማርያም የፀነሰችው ሥግው ቃለ እግዚአብሔርን ነው። እግዚአብሔር ቃልም በእውነት ከድንግል ተወለደ፣ የለበሰውም ሥጋ ለእኛ [ለሰዎች] ያለንን ሁሉ ያለው ነው፤›› (ወደ ትራልዮን ሰዎች ምዕራፍ ፲)።

ይህም የሚያሳየን ለሰዎች መዳን የእግዚአብሔር ቃል ከሰማይ መውረድና ከድንግል መወለድ ብቻ ሳይኾን የክርስቶስ ፍጹም አምላክ ሳለ ፍጹም ሰው መኾን አስፈላጊ ነው። አስቀድመን የጠቀስነው ሊቅ ትምህርቱን ሲያጠናክረውም ‹‹ሕፃናትን በማኅፀን የሚሠራቸው እርሱ በማኅፀን አደረ፣ ከድንግል ሥጋና ነፍስን ነሥቶ ያለ ወንድ ዘር አምላክ ሳለ ሰው ኾነ›› በማለት ክርስቶስ የተዋሐደው ሥጋ ከድንግል የነሣው ፍጹም የሰው ልጆች ሥጋ መኾኑን አረጋግጦልናል። ቅዱስ አግናጥዮስስ በመልእክቱ ላስተማራቸውም ይህ እውነት ባይኾን ኖሮ ራሱን ለተራቡ የበረሃ አናብስት የሚሰጥ ሞኝ እንዳልኾነ በማስረገጥ ያዳነው እና የሚያመልከው ክርስቶስ ፍጹም አምላክ፣ ፍጹም ሰው መኾኑን ያስረዳቸዋል (ዝኒ ከማሁ)፡፡

ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫም የ‹‹ለፌ እማርያም›› የእግዚአብሔር ወልድን ቅድምና በሚያመሠጥርበት እና አስተማሪውን ፎጢኖስን በሚዘልፍበት አንቀጹ የሥጋዌን ምሥጢር እንዲህ በማለት አስቀምጦልናል፤ ‹‹ዳግመኛም ድንግል መልአኩን እንዳልኸኝ ይኹንልኝ አለችው። ያን ጊዜም ቃል ከእርሷ ሥጋን ተዋሐደ [ሥጋን ነሣ] … በዚያ [በሰማይ] በአባቱ ቀኝ አለ፤ በዚህም [በምድር] በእናቱ ማኅፀን ውስጥ አለ። … በዚያ ያለ እናት አባት አለው፤ በዚህም ያለ ምድራዊ አባት እናት አለው። በዚያ ገብርኤል በፍርሃት ይቆማል፣ በዚህም ገብርኤል በሐሴት የምሥራች ይናገራል፤ በዚያ በጽርሐ አርያም የሚደነቅ ከማይታይ አብ የመወለድ ምስጋና፤ በዚህም በቤተ ልሔም የሚደነቅ ከድንግል የመወለድ ምስጋና … በሰው መጠን ጐልማሳ ባይኾን፣ በሰው ልጆችም አካል ባይገለጥ እኛን ስለ ማዳን ማን መከራ በተቀበለ ነበር። እነሆ  ከሰማይ ትጉሃን ይልቅ የሰው ልጅ ከበረ፤ እግዚአብሔር ከሴት (ከእመቤታችን) ተወልዷልና፤›› (መጽሐፈ ምሥጢር፣ የልደት ምንባብ)።

የድኅነት ወይም የሰው ልጆች መክበር እና የሥጋዌን የጠበቀ ቍርኝት ተመለከታችሁ! እነዚህ ቅዱሳን አበው የሚነግሩን እግዚአብሔር ሰውን ለማዳን ሰው ባይኾን የሰው ልጆች ድኅነት ጥያቄ ውስጥ ይገባ እንደ ነበር ነው። አግናጥዮስ ‹‹እግዚአብሔር ፍጹም ሰው ባይኾን ሞቴ ከንቱ በኾነ››፤ አባ ጊዮርጊስም ‹‹እግዚአብሔር በሰው ሥጋ ባይገለጥ ማን ባዳነን?›› በማለት የክርስቶስን ሥጋዌ የድኅነተ ሰብእ ቍልፍ መለኮታዊ ተግባር መኾኑን ያስረዳሉ።

ይቆየን

የ፳፻፱ ዓ.ም በዓለ ልደትን በማስመልከት ቅዱስ ፓትርያርኩ የሰጡት ቃለ ምዕዳን

ታኅሣሥ ፳፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

dscn6280

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

 

ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ዘተናገረ በእንተ በዓለ ልደቱ ለእግዚእነ ወአምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ሎቱ ስብሐት!!

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!

  • በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፤
  • ከሀገር ውጪ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፤
  • የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤
  • በሕመም ምክንያት በየፀበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤
  • እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፤

እኛን ለማዳን በለበሰው ሥጋ በቤተ ልሔም ተወልዶ በመካላችን የተገኘው፣ በመለኮታዊ ባህርዩ የማይወሰነው አካላዊ ቃል እግዚአብሔር ወልድ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንኳን ለሁለት ሺሕ ዘጠኝ ዓመተ ምሕረት በዓለ ልደቱ በሰላም አደረሳችሁ!!

“ወበዘርዕከ ይትባረኩ ኵሎሙ አሕዛበ ምድር፤ የምድር አሕዛብ ሁሉ በዘርህ ይባረከሉ፤” (ዘፍ ፳፪፤ ፲፰)፡፡

በሁሉም ዘንድ እንደሚታወቀው በረከት የመልካም ነገር ሁሉ ምንጭ ነው፤ እግዚአብሔር በጥንተ ፍጥረት ለሰው ልጅ የሰጠው የመጀመሪያው ጸጋ ብዝኃ በረከት ነው፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ ይህንን አስመልክቶ እንዲህ ይላል “እግዚአብሔርም ባረካቸው፤ እንዲህም አላቸው፤ ብዙ ተባዙ ምድርንም ሙሉአት፤ ግዙአትም፤ የባህርን ዓሣዎችና የሰማይን ወፎች በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ግዙአቸው” ይላል ፤ (ዘፍ ፩፤ ፳፰)፡፡

ለሰው የተሰጠው በረከት በኃጢአት ምክንያት መሰናክል ቢገጥመውም፣ እግዚአብሔር በፍጡሩ ጨርሶ አይጨክንምና ሙሉና ፍጹም የሆነው በረከት እንደገና ተመልሶ ለሰው ልጅ እንዴት እንደሚሰጥ ለበረከት በጠራቸውና በመረጣቸው ቅዱሳን አበው አማካይነት ሲያስታውቅ ኖሮአል፡፡

በተለይም የበረከት አባት ተብሎ በሚታወቀው በአብርሃም ዘር በኩል መጻኢው በረከት እውን እንደሚሆን “በዘርህ የምድር አሕዛብ ሁሉ ይባካሉ” ተብሎ በእግዚአብሔር አንደበት በማያሻማ ሁኔታ ተነግሮ ነበር፡፡

ከእውነተኛው በረከት ተራቁታ የቆየችው ዓለመ – ሰብእ፣ እግዚአብሔር በራሱ ቃል የገባላት ዘላቂውና እውነተኛው በረከት እስኪመለስላት ድረስ ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዓመታት በተስፋ ስትጠባበቅ ቆይታለች፡፡

የተናረውን የማያስቀር እግዚአብሔር በረከቱን ለሕዝቡ የሚያድልበት ጊዜ ሲደርስ ቅዱስ መንፈሱን ባሳደረባት ቅድስት እናት በኤልሳቤጥ አንደበት የበረከቱ ሙዳይ ቅድስት ድንግል ማርያም፣ በረከቱ ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑንና በረከቱን ለምድር አሕዛብ ሁሉ ሊያድል እንደመጣ “ከሴቶች ሁሉ ተለይተሽ አንቺ የተባረክሽ ነሽ የማኅፀንሽ ፍሬም የተባከ ነው” ሲል የምሥራቹን ለዓለም አሰማ፤ (ሉቃ ፩፡፵፩-፵፫)፡፡

ቀዳማዊ የሆነ እግዚአብሔር ወልድ በድንግል ማርያም ማኅፀን ውስጥ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በፅንስ ቆይቶ የዛሬ ሁለት ሺሕ ዘጠኝ ዓመተ ምሕረት ታኅሣሥ ሃያ ዘጠኝ ቀን በቤተ ልሄም ተወለደ፡፡ ጌታችን በተወለደ ጊዜ የሰማይ ሠራዊት ማለትም መላእክትና የመላእክት አለቆች “ወናሁ ተወልደ ለክሙ መድኅን ዘውእቱ እግዚእ ቡሩክ፤ እነሆ መድኅን ተወልዶላችኋል፤ ይኸውም ቡሩክ የሆነ ጌታ ነው” በማለት የሕጻኑን ማንነት ከገለጹ በኋላ “በሰማያት ለእግዚአብሔር ክብር ይሁን፤ በምድርም ሰላም ይሁን፤ ለሰውም በጎ ፈቃድ ይደረግለት” እያሉ የተወለደው ሕጻን ለሰው ልጅ የሚያስገኘውን ሰላምና መልካም በረከት በመግለጽ ደስታቸውን በቃለ መዝሙር በቤተ ልሄም ዙሪያ አስተጋብተዋል፡፡

ከሰው ወገንም ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ከእርስዋ ጋር የነበሩ ወገኖች፣ እንደዚሁም በአካባቢው የነበሩ የከብት እረኞች በመላእክት የምስጋና መዝሙር ተሳታፊዎች ነበሩ፤ (ሉቃ ፪፤፰-፳)፡፡

እንግዲህ ከጥንት ጀምሮ በአበው ሲነገርና ሲጠበቅ የነበረው የበረከት ተስፋ በቃልም፣ በመልእክትም፣ በሐሳብም፣ በምሥጢርም ተፋልሶ ሳያጋጥመው፣ ከላይ ጀምሮ እስከ ታች ፍሰቱና ምሥጢሩ ተጠብቆ በተነገረው መሠረት ተፈጽሞ መገኘቱ፣ የክርስትና ሃይማኖት ምን ያህል አምላካዊ የሆነ ጽኑ መሠረት እንዳለው ያረጋግጣል፡፡

የክርስትና ሃይማኖት መሠረቱ “ባርኮ እባርከከ፤ መባረክን እባርክሃለሁ” ከሚል ተነሥቶ፣ “የአባቴ ቡሩካን መንግሥተ ሰማያትን ትወርሱ ዘንድ ወደኔ ኑ!” በሚል የሚጠናቀቅ፣ መነሻውና መድረሻው በረከት የሆነ ሃይማኖት ነው፡፡

የክርስትና ሃይማኖት “ለሰላሙም ፍጻሜ የለውም” ከሚል ተነሥቶ “በምድርም ሰላም ይሁን” በሚል ተንደርድሮ፣ በምስጋና፣ በክብርና በሰላም፣ በማያልፍም ሕይወት ዘላለማዊነቱን የሚያውጅ ሃይማኖት ነው፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደበት ዕለት ከወደላይ የተላለፈው ዓቢይ መልእክት ሰላምና በረከት በምድር ላይ ሆነ የሚል እንደሆነ ማስተዋል አለብን፡፡

ታላቁ ሊቅና ኢትዮጵያዊው አባት ቅዱስ ያሬድ ስለዚህ በረከት ሲናገር “በእንተ ልደቱ ለክርስቶስ አድባር ኮኑ ኅብስተ ሕይወት፤ ወዕፀወ ገዳምኒ ፈረዩ አስካለ በረከት፤ ወማየ ባህርኒ ኮነት ሐሊበ ወመዓረ፤ ማለትም ክርስቶስ በተወለደ ጊዜ ተራሮች የሕይወት እንጀራ ሆኑ፤ የበረሀ ዛፎችም የበረከት እሸትን አፈሩ፤ የባህር ውሀም ወተትና ማር ሆነች” ይላል፡፡

የቅዱስ ያሬድ ቃለ ዝማሬ ሕያዋኑም ግኡዛኑም ሁሉ በልደተ ክርስቶስ ምክንያት በበረከት እንደ ተንበሸበሹ ይመሰክራል፡፡

ከዚህ አኳያ በበዓለ ልደተ ክርስቶስ የሚበላ እንጀራና የሚጠጣ ውሃ አጥቶ በረኃብና በጥም ተጐሳቊሎ የዋለ አልነበረም ብቻ ሳይሆን፤ እንጀራውም ወተቱም ማሩም ፍጥረቱ ሁሉ እንደ ፈለገው እየተመገበ በሰላምና በደስታ ቀኑን ሁሉ ማሳለፉን እንገነዘባለን፡፡

የልደተ ክርስቶስ በረከት ገደብ የለሽ መሆኑን ያወቅን የኢየሱስ ክርስቶስ ተከታዮች ነን የምንል ክርስቲየኖች በዚህ ቀን ርቦትና ጠምቶት፣ አዝኖና ተክዞ የሚውል ሰው እንዳይኖር ያለውን በማካፈልና በጋራ በመመገብ የታረዘውን በማልበስ የታመመውን በመጠየቅ የበዓሉን ሃይማኖታዊና ሥነ ምግባራዊ ገጽታ መጠበቅና ማስጠበቅ ይኖርብናል፡፡

በዓለ ልደተ ክርስቶስ የበረከት ቀን ከመሆኑም ሌላ የዕርቅ፣ የእኩልነትና የአንድነት በዓልም ነው፡፡ ከብዙ ጊዜ መለያየትና መራራቅ በኋላ፣ ፈጣሪ የሰዎችን ሥጋ አካሉ አድርጎ በሰዎች መካከል በአካል መገኘት ከዕርቅ ሁሉ የበለጠ ዕርቅ መሆኑን መዘንጋት የለበትም፡፡

በዕለተ ልደት ክርስቶስ መላእክትና ሰዎች ፈጣሪያቸው በተወለደበት ዙሪያ ተሰባስበው በእኩልነትና በአንድነት ሲዘምሩና ሲያመሰግኑ ማየትና መስማትም የፍጡራንን እኩለነትና አንድነት ያረጋገጠ ሌላው ክሥተት ነበረ፡፡

ሰማያውያንና ምድራውያን ለሰው ልጅ ህልውና ወሳኝ የሆነውን “ሰላም በምድር ይሁን” እያሉ በአንድ ቃል መዘመራቸውም ለሰማያውያኑም ሆነ ለምድራውያኑ ከሰላም የበለጠ ትልቅ ጸጋ የሌለ መሆኑን የሚያስገነዝብ ነበረ፡፡

እንዲህም ስለሆነ ከልደተ ክርስቶስ ያልተማርነው ትምህርት የለም ማለት ይቻላል፤ እግዚአብሔር በልደተ ክርስቶስ ዕለት ያስተማረን ብቻ አጥብቀን ብንይዝና ይህንኑ ብንፈጽም ከበቂ በላይ ነው ቢባል ፍጹም እውነት ነው፡፡

ተራራው ሁሉ የሕይወት እንጀራ ሆነ፤ የበረሀ ዛፍ ሁሉ የበረከት እሸት ሆነ፤ የባህር ውሃም ማርና ወተት ሆነች ተብሎ ሲነገር በዓለ ልደተ ክርስቶስ የልማት፣ የዕድገትና የብልፅግና አስተማሪ መሆኑን ያስገነዝባል፡፡

ከዚህ አንጻር ዛሬም ቤተ ክርስቲያን የምታስተምረው ተራራው ይልማ፣ በረሀው በደን ይሸፈን፣ ውሃው ከብክለት ድኖ ለምግብነት የሚያገለግሉ ሕይወታውያን ፍጡራን በብዛት ይኑሩበት የሚለው በልማትና በበረከት የተሞላው የልደተ ክርስቶስ አስተምህሮ ነው፤ ሕዝበ ክርስቲያኑ ይህንን አምላካዊ አስተምህሮ በምልአት ተቀብሎ ወደ ልማት ከተሠማራ በዚያው መጠን በረከቱን በገፍ ያፍሳል፡፡

ከዚህም ጋር “የሺሕ ፍልጥ ማሠሪያው ልጥ” እንደሚባለው የሁሉም ማሠሪያ ሰላም ስለሆነ የድሮ ነጋዴ ለንግድ ሲወጣ ስንቁን በትከሻው ተሸክሞ እንደሚጓዝ ሁሉ፣ ዛሬም የልማት ነጋዴ ሕዝባችን ሰላምን በልቡ ቋጥሮ መጓዝ ይኖርበታል፡፡

ሁሉም ችግሮች ከሰላም በታች መሆናቸውን ሁሉም ማኅበረሳባችን መገንዘብ አለበት፤ ሁሉም ለአንድነት፣ ለእኩልነት፣ ለፍትሕ ለወንድማማችነት፣ ለመተማመንና ለመከባበር መስፈን የማያወላውል አቋም ሊይዝ ይገባል፡፡

የቀደሙት አባቶቻችን ኢትዮጵያን ታላቅ ሀገር እንድትሆን ያበቋት አንድነታቸውን ጠብቀው በጋራ ስለሠሩ ነው፤ ያለ አንድነት ታላቅነትም፣ ኃያልነትም፣ ልማትና ዕድገትም፣ ፈጽሞ እንደማይገኝ ሳይታለም የተፈታ ነውና ሕዝባችን ይህንን በውል ማጤን ይኖርበታል፡፡

በመጨረሻም

ከላይ ለመግለፅ እንደተሞከረው የክርስቶስ መወለድ ዋና ዓላማ መለያየትና መቃቃርን፣ መነታረክንና፣ በጥላቻ ዓይን መተያየትን አስወግዶ በምትኩ ዕርቅን፣ ዘላቂ ሰላምና አንድነትን በሰው ሁሉ አእምሮ ውስጥ ማስፈን እንደሆነ እናውቃለን፡፡

በመሆኑም ይህ ነገረ ሕይወት ከተሰበከባቸው የዓላማችን ሀገራት ኢትዮጵያ ቀዳሚዋ ሀገር እንደመሆኗ መጠን፣ በእግዚአብሔር ከተሰጣት የቅድሚያ ኃላፊነት አንጻር በሀገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ደረጃም ሁሉ፣ እንደ ድሮው ደማቁ የአንድነት ታሪኳና ተደናቂው ሥልጣኔዋ፣ እንደዚሁም ጽኑ ሰላምዋና ልማቷን ጠብቃ በማስጠበቅ አስተማሪነትዋ ጎልቶ እንዲወጣ “ችግሮች ሁሉ ከሰላም በታች ናቸው” የሚለውን ጠንካራ የሰላም አስተሳሰብ መርሕ በማድረግ ሁሉም በአንድነት፣ በኃለፊነት፣ በቅንነትና በተቈርቋሪነት ሀገሩን እንዲጠብቅና እንዲያለማ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

መልካም የልደት በዓል ያድርግልን

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝባችንን ይባርክልን

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

አሜን

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፤

ታሕሣሥ ፳፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ የእሳት ቃጠሎ ደረሰበት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ታኅሣሥ ፳፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

sebeta

የተቃጠለው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ወለልና የሕንጻው ቍሳቍስ በከፊል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሰበታ ወረዳ ቤተ ክህነት የሚገኘውና በጥር ወር ፳፻፮ ዓ.ም የተመሠረተው የሰበታ ዋታ ምዕራፈ ቅዱሳን አቡነ አረጋዊ እና በዓታ ለማርያም ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ታኅሣሥ ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከጠዋቱ ፪ ሰዓት ከ፴ ደቂቃ አካባቢ የእሳት ቃጠሎ ደረሰበት፡፡

ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ በቆርቆሮና በኮምፖርሳቶ ከመታነጹ በተጨማሪ ቃጠሎው የደረሰው ካህናቱ አገልግሎታቸውን ፈጽመው ከቤተ ክርስቲያን ከወጡ በኋላ መኾኑ ጉዳቱን የከፋ አድርጎታል፡፡

የቃጠሎው መንሥኤ እስካሁን በግልጽ እንዳልታወቀና በቃጠሎውም ከጽላቶቹ በስተቀር ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ሙሉ በሙሉ እንደ ወደመ የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ መልአከ ሕይወት ሐዋዝ ተስፋ ለማኅበረ ቅዱሳን ሚድያ ክፍል አስታውቀዋል፡፡ እንደ አስተዳዳሪው ገለጻ ከአምስት መቶ ሺሕ ሰማንያ ብር በላይ የሚገመቱ ንዋያተ ቅድሳት በቃጠሎው ወድመዋል፡፡

sebeta-copy

በቃጠሎው የወደሙ ንዋያተ ቅደሳት በከፊል

የማኅበረ ቅዱሳን ጋዜጠኞች ቦታው ድረስ በመሔድ እንደ ተመለከትነው ታኅሣሥ ፳፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ረፋድ ላይ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በደብሩ ተገኝተው ማኅበረ ካህናቱንና ሕዝበ ክርስቲያኑን አጽናንተዋል፤ የደብሩን ይዞታ የሚያስከብርና ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑን የሚያስገነባ የልማት ኰሚቴም አስመርጠዋል፡፡ እንደዚሁም የሰበታ ወረዳ ቤተ ክህነት ሠራተኞች፣ የየአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ካህናትና ማኅበረ ምእመናን ለሕንጻው ማሠሪያና ለንዋያተ ቅድሳት መግዣ የሚኾን ገንዘብ በማሰባሰብ ለልማት ኰሚቴው አበርክተዋል፡፡

አቡነ ሳዊሮስ

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ

ብፁዕነታቸው በዕለቱ ቃለ ምዕዳን ሲሰጡ የልማት ኰሚቴው ከሐሜት በጸዳ መልኩ የማያድግምና ዘላቂ የኾነ ሥራ መሥራት እንደሚጠበቅበት ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም ለሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ግንባታ ብቻ ሳይኾን ለሃይማኖታችን መጠበቅና ለምእመናን አንድነትም ዘብ መቆም ይገባዋል ብለዋል፡፡

‹‹ይህ ዅሉ የደረሰው በእኛ ኀጢአት ነው›› ያሉት ብፁዕነታቸው የደብሩ አገልጋይ ካህናትና የአካባቢው ምእመናን ጥላቻንና መለያየትን በማስወገድ፤ ከኀጢአት በመራቅ፤ በፍቅር፣ በሰላምና በአንድነት በመኾን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በቅንነት እንዲያገለግሉ አባታዊ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በቃለ ምዕዳናቸው ማጠቃለያም በደብሩ ላይ የደረሰውን የእሳት ቃጠሎ ከማጥፋት ጀምሮ መቃኞ ቤት በመሥራትና በሌላም ልዩ ልዩ መንገድ ድጋፍና ትብብር ያደረጉትን ምእመናንና በአካባቢው የሚኖሩ የእስልምና እምነት ተከታዮችን አመስግነዋል፡፡

መቃኞ

በአካባቢው ነዋሪዎች ትብብር የታነጸው መቃኞ ቤት

በቤተ ክርስቲያኑ ላይ የደረሰውን የቃጠሎ አደጋ ሰበካ ጉባኤው ለፖሊስ ሪፖርት እንዳደረገና በቃጠሎው ዕለትም የሰበታ ወረዳ ኮማንድ ፖስት፣ የጸጥታ ዘርፍ ሠራተኞችና ሌሎችም የመንግሥት ባለሥልጣናት እንደ ተገኙ የተናገሩት አስተዳዳሪው የቃጠሎው መንሥኤ እስኪጣራ ድረስም የደብሩ ሰሞነኛ ካህናትና የጥበቃ ሠራተኞች በሕግ ከለላ ሥር ይገኛሉ ብለዋል፡፡

አማንያንም ኾኑ ኢአማንያን የአካባቢው ነዋሪዎች በጋራ በመረባረብ ለታቦተ ሕጉ መቀመጫ የሚኾን ጊዜያዊ መቃኞ ቤት ማነጻቸውን ያስታወቁት የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ እንደ ገና ታድሶ አገልግሎት ይሰጥ ዘንድም የመላው ሕዝበ ክርስቲያን ድጋፍና ርዳታ አይለየን ሲሉ በቤተ ክርስቲያን ስም ጥሪያቸውን ያቀርባሉ፡፡

ትውልዱን ከሱስ ለመታደግ የቤተ ክርስቲያን ሚና

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ታኅሣሥ ፳፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል አማካይነት በተዘጋጀው የዐውደ ጥናት ጉባኤ ታኅሣሥ ፳፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በማኅበሩ ሕንጻ ፫ኛ ፎቅ አዳራሽ በቀረበው ጥናታዊ ጽሑፍ ከሱስ የነጻ ትውልድ ለመፍጠር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሚና ከፍተኛ መኾኑ ተገለጸ፡፡

ዶ/ር

ዶክተር ጃራ ሰማ ጥናታዊ ጽሑፍ አቅራቢ

በጉባኤው ‹‹ከሱስ የነጻ ትውልድ ለመፍጠር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሚና›› በሚል ርእስ ጥናታዊ ጽሑፋቸውን ያቀረቡት የሕክምና እና የማኅበራዊ ሳይንስ ባለሙያው ዶክተር ጃራ ሰማ የአልኮል መጠጦች፣ አደንዛዥ ዕፀዋት፣ አሽሽ፣ ትንባሆ፣ ሻይ፣ ቡና፣ የለስላሳ መጠጦች፣ ልዩ ልዩ መድኀኒቶችና የመሳሰሉት ልምዶች፤ እንደዚሁም የኢንተርኔት አገልግሎት፤ በተመሳሳይ መልኩ ሰዶማዊነት፣ ወደ ዝሙት ተግባር የሚወስዱ ፊልሞችን በዓይን ማየትና በድምፅ መስማት፣ እንደዚሁም ራስን ለፍትወተ ሥጋ ማነሣሣት በተደጋጋሚና በብዛት ከተወሰዱ ወይም ከተተገበሩ ሱስ ሊያስይዙ እንደሚችሉ ጠቁመዋል፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም ሳውና ባዝ፣ ስቲም ባዝና ሞሮኮ ባዝን ጨምሮ ሌሎች የመታሻ ሥፍራዎችና ጂም ቤቶችም ሱስን ሊያስይዙ የሚችሉ የምቾትና የድሎት አገልግሎቶች መኾናቸውን ጥናት አቅራቢው አስረድተዋል፡፡ ሱስ በድርጊት በመፈጸምና በመቅመስ ብቻ ሳይኾን በማየት፣ በመስማት፣ በመዳሰስ ወይም በመንካት እንደሚፈጸም ያስረዱት ጥናት አቅራቢው በማሽተት ከሚፈጸሙ ሱስ አምጪ ተግባራት መካከልም ቤንዚን፣ ትምባሆ፣ ሲጋራና ማስቲሽ የማሽተት ሱስን እንደ ምሳሌ አድርገው አቅርበዋል፡፡

ሱስ የሰውን ልጅ አእምሮውንና አካሉን በአግባቡ የማይጠቀም፤ የፈዘዘ፣ የደነዘዘ እንዲኾን ያደርጋል ያሉት ባለሙያው ሱሰኝነት ትዳር እንዲፈርስ፣ ቤተሰብ እንዲበተን፣ ክርስቲያናዊ ሕይወት እንዲላላ፣ የማይታመን ራእይ አየን የሚሉ የሐሰት ባሕታውያን እንዲበዙ፣ ሽብርተኝነት እንዲስፋፋ፣ ወዘተ. በማድረግ ከግለሰብ ጀምሮ በቤተ ክርስቲያንና በአገር ላይ የሚያደርሰው ሃይማኖታዊ፣ ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊና ምጣኔ ሀብታዊ ጉዳት ከፍተኛ መኾኑን አስገንዝበዋል፡፡

የአእምሮ መታወክ፣ ጭንቀትና ውጥረት፣ የአስተዳደግ ችግር፣ የጓደኛ ተፅዕኖ፣ ቤተሰባዊ ግጭት፣ ሴሰኝነት፣ በኑሮ የሚያጋጥም ዕዳና ኪሳራ፣ ሥራ አጥነት፣ ወዘተ የመሳሰሉት አጋጣሚዎች ለሱስ የሚዳርጉ መሠረታዊ ጫናዎች መኾናቸውን ያመላከተው የዶ/ር ጃራ ጥናት ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብ፣ የግብረ ገብ ትምህርቶችን በመማርና ሥልጠናዎችን በመውሰድ አመለካከትን መለወጥ (የእይታ አድማስን ማስፋት)፤ እንደዚሁም ማኅበራዊ ግንኙነትን ማሳመርና ሓላፊነትን ማሳደግ ከሱስ የማምለጫ መንገዶች መኾናቸውን ያስረዳል፡፡

tinat

የጥናቱ ታዳሚዎች በከፊል

የሰው ልጅ ከአምላኩ ውጪ በእርሱ ላይ አንዳች ኃይል ሊሠለጥንበት የማይችል በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠረ ከፍጡራን ዅሉ የላቀ ክቡር ፍጥረት መኾኑን በጥናታቸው ያስታወሱት ዶ/ር ጃራ ሰማ የሰው ልጅ ክብሩን አዋርዶ ይሠለጥንባቸው ዘንድ የተሰጡት ፍጥረታት በእርሱ ላይ እንዲሠለጥኑ ከፈቀደ በምድር በኀጢአት አረንቋ ወድቆ እንደሚኖር፤ በዚህም ራሱን እንደሚበድልና የፈጠረውን አምላክም እንደሚያሳዝን ገልጸው ትውልዱ የተፈጠረለትን ዓላማ በመረዳት ወደ ሱስ ከሚወስዱ ነገሮች ራሱን መጠበቅ እንዳለበት አስገንዝበዋል፡፡

ምእመናንን ከልጅነታቸው ጀምሮ በሰንበት ት/ቤት፣ በማኅበር፣ በዐውደ ምሕረት፣ በኅትመት ውጤቶችና በሌላም ልዩ ልዩ መንገድ ግብረ ገብነትን በማስተማር፤ ወደ ሱስ የገቡትንም በሱባዔ፣ በቀኖና፣ በንስሐ፣ በጠበልና በሥጋ ወደሙ አማካይነት ፈውስን እንዲያገኙና በመንፈሳዊውም ኾነ በዓለማዊው ሕይወታቸው ጤናማ ኾነው እንዲኖሩ በማድረግ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ያበረከተችው ሚና ከፍተኛ መኾኑን የጠቀሱት ጥናት አቅራቢው ችግሩን በዘላቂነት ለመከላከል የተዘጋጀ መዋቅራዊ አደረጃጀት ባለመኖሩ፣ ካህናት ከሕክምና ባለሙያዎች ጋር ተቀናጅተው ባለመሥራታቸው፣ ሱሰኞች ከሱስ ከወጡ በኋላ የሚቋቋሙበት ተቋም ባለመመሥረቱ፣ በጉዳዩ ላይ በቂ ጥናትና ምርምር ባለመደረጉ፣ የሚድያ ሽፋን ባለማግኘቱና በጀት ባለመመደቡ የተነሣ ቤተ ክርስቲያናችን ሓላፊነቷን በአግባቡ እንዳትወጣ ካደረጓት ምክንያቶች መኾነቻውን በጥናታቸው ዳሰዋል፡፡

ዶ/ር ጃራ ሰማ በጥናታቸው ማጠቃለያም ‹‹ምእመናን በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ብቻ ሳይኾን በማኅበራዊ ኑሯቸውም ከሌሎች ጋር ተስማምተው በፍቅር፣ በቅንነት፣ በሰላምና በአንድነት እንዲኖሩ የማስቻል ከማንም በላይ ከአምላክ ዘንድ የተሰጣት መንጋዋን ከጥፋት የመጠበቅ ከፍተኛ ሓላፊነት እንዳለባት ቤተ ክርስቲያናችን ተገንዝባ የአሠራር ችግሮችን በመቅረፍ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ትኩረት ሰጥታ መሥራት ይገባታል›› ብለዋል፡፡

ዝክረ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ጻድቅ

ታኅሣሥ ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

t

ቅዱሳን ጻድቃን በመንፈሳዊ አርአያነታቸው፣ በጸሎታቸውና በትምህርታቸው ከከበቡን የነፍስ ጠላቶች፤ ከርኲሳን መናፍስትና ከጨለማው ልጆች፣ ከክፉ ሰዎች ሽንገላና ተንኰል ለመሰወርና ለመጠበቅ ከእግዚአብሔር የተቀበሉት ሥልጣን ምን ጊዜም ይሠራል፡፡ በጻድቃን መኖር ሀገር ከጥፋት ትድናለች፡፡ የጻድቃንን ስም ጠርቶ እግዚአብሔርን በመለመን በረከትና ረድኤት ይገኛል፡፡ ስለ ጻድቃን ብሎ እግዚአብሔርም ምሕረቱን ያድላል፡፡ ጻድቃንን ማሰብ ሥራቸውን መዘከር ክርስቲያናዊ ሕይወታችንን ያጐለምሳል፡፡ በነፍስ በሥጋ ይታደገናል፤ ይረባናል፤ ይጠቅመናል፡፡

ስለዚህም ነው ቤተ ክርስቲያናችን ጻድቃንን እንድናስባቸው፣ በስማቸውም ለድሆችና ለጦም አዳሮች እንድንመጸውት፣ መታሰቢያቸውን እንድናደርግ የምትመክረን፤ የምታስተምረን /ማቴ.፲፥፵፩-፵፪/፡፡ ቅዱሳን ጻድቃን በሕይወተ ሥጋ ሳሉም ኾነ ከሞቱ በኋላ በዐጸደ ነፍስ ኾነው በጸሎታቸው ለሚታመኑ፣ በቃል ኪዳናቸው ለሚማጸኑ ምእመናን በመጸለይና ወደ እግዚአብሔር በማማለድ ድኅነተ ሥጋ፣ የድኅነት ነፍስን የሚያስገኙልን የችግር ጊዜ አማላጆቻችንና አስታራቂዎቻን ናቸው፡፡ ከእነዚህ ቅዱሳን መካከል ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንደኛው ናቸው፡፡

‹ተክል› ማለት ፍሬያማ ዕንጨት፣ ዛፍ፣ ቅመም፣ ቅጠላ ቅጠል፣ የሚበላ፣ የሚሸተት፣ ገነታዊ ዕፅ፣ እንዲሁም ሕግ ሥርዓት ማለት ነው /ማቴ.፲፭፥፲፫/፡፡ ‹ሃይማኖት› ማለት ደግሞ በሀልዎተ እግዚአብሔር፣ እግዚአብሔር የዅሉ አስገኚ መኾኑን፣ በሥላሴ አንድነትና ሦስትነት፣ በቅዱሳን ተራዳኢነት ማመን አምኖም መመስከር ማለት ሲኾን ተክለ ‹ሃይማኖት› የሚለው ሐረግም የሃይማኖት ተክል፣ ይኸውም የጽድቅ ፍሬን ያፈራ፣ ከኃጢአት ሐሩር ማምለጫ ዛፍ፣ ምእመናንን በቃለ ወንጌል ያጣፈጠ ቅመም፣ መዓዛ ሕይወቱ የሚማርክ፣ ቢመገቡት ረኃበ ነፍስን የሚያስወግድ ቅጠል፣ የጻድቃን መጠለያ ዕፅ የሚል ትርጕም አለው፡፡ ገድለ ተክለ ሃይማኖትም ‹‹ተክለ ሃይማኖት ማለት የአብ፣ የወልድ፣ የመንፈስ ቅዱስ ተክል ማለት ነው›› ሲል የጻድቁን ስም ይተረጕመዋል፡፡

ጻድቁ አባታችን ሕይወታቸዉን ሙሉ ለእግዚአብሔር በመስጠት፣ እንደ በሬ ተጠምደው፣ እንደ ገበሬ ታጥቀው፣ ይህንን ዓለም ንቀው፣ በጾም በጸሎት ተወስነው በብሕትውና በመኖራቸው፤ እርሳቸው በአሚነ ሥላሴ ጸንተው ሌሎችንም እንዲጸኑና እንዲያምኑ በማድረጋቸው፤ እንደዚሁም እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ወንጌልን በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ በመስበክ በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ድውያነ ሥጋን በተአምራት፣ ድውያነ ነፍስን በትምህርት የፈወሱ ሰባኬ ወንጌል በመኾናቸው ‹‹ተክለ ሃይማኖት›› ተብለው ይጠራሉ፡፡

አቡነ ተክለ ሃይማኖት በእግዚአብሔር ድንቅ ጥበብ፣ በሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ብሥራት፤ በኢትዮጵያ ምድር በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ልዩ ስሙ ኢቲሳ በሚባል ቦታ ከአባታቸው ከካህኑ ጸጋ ዘአብና ከእናታቸው ከቅድስት እግዚእ ኀረያ መጋቢት ፳፬ ቀን ተፀንሰው ታኅሣሥ ፳፬ ቀን ፲፪፻፲፪ ዓ.ም ተወለዱ፡፡ በተወለዱ በሦስተኛው ቀን እሑድ ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት ከእናታቸው ዕቅፍ ወርደው ‹‹አሐዱ አብ ቅዱስ፤ አሐዱ ወልድ ቅዱስ፤ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ፤ አንዱ አብ ቅዱስ ነው፤ አንዱ ወልድ ቅዱስ ነው፤ አንዱ መንፈስ ቅዱስ ቅዱስ ነው›› በማለት ሥላሴን አመስግነዋል፡፡ ወላጆቻቸው ያወጡላቸው ስም ‹‹ፍሥሐ ጽዮን›› የሚል ሲኾን ‹‹ተክለ ሃይማኖት›› ደግሞ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ሚካኤል ያወጣላቸው ስም ነው፡፡ በተወለዱ በ፲፭ ዓመታቸው ዲቊናን፤ በ፳፪ ዓመታቸው ደግሞ ቅስናን ከግብፃዊው ጳጳስ ከአባ ጌርሎስ (ቄርሎስ) ተቀብለዋል፡፡

አንድ ቀን ወደ ጫካ ለአደን በሔዱበት ዕለት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱ ክርስቶስ ተገልጦላቸው ጸጋ መንፈስ ቅዱን ካሰደረባቸው፤ እንደዚሁም ሐዲስ ሐዋርያ› ብሎ ወንጌል ወዳልተዳረሰበት ቦታ እንደሚልካቸው ከነገራቸው፤ ቅዱስ ሚካኤልም ከአውሬ አዳኝነት ሰውን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመመለስ እንደ ተመረጡና አጋንንትን የማውጣት፣ ተአምራትን የማድረግ ሥልጣን እንደ ተሰጣቸው፤ ስማቸውም ተክለ ሃይማኖት እንደሚባልና ትርጓሜውም ተክለ አብ፣ ተክለ ወልድ፣ ተክለ መንፈስ ቅዱስ ማለት እንደ ኾነ ካስረዳቸው በኋላ ወደ ቤታቸው ተመልሰው ያላቸውን ንብረት ኹሉ ለቤተ ክርስቲያንና ለነዳያን ሰጥተው ‹‹አቤቱ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! የመንግሥተ ሰማያትን በር ትከፍትልኝ ዘንድ እነሆ ቤቴን እንደ ተከፈተ ተውኩልህ›› በማለት ቤታቸውን ትተው ወንጌልን ለማስተማር ፈጥነው ወጡ፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምረው በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ ወንጌልን በመስበክና ተአምራትን በማድረግ ብዙ አሕዛብን ከአምልኮተ ጣዖት ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር፤ ከገቢረ ኀጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ መልሰዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንንም አንጸዋል፡፡ ‹ሐዲስ ሐዋርያ› የተባሉትም በዚህ ተልእኳቸው ሲኾን፣ ትርጕሙም ሐዲስ ኪዳንን ወይም ሕገ ወንጌልን እየተዘዋወረ የሚያስተምር ሰባኬ ወንጌል፤ በክርስቶስ ስም ድንቅ ድንቅ ተአምራትን የሚደርግ የክርስቶስ ተከታይ (ሐዋርያ) ማለት ነው፡፡

በአጠቃላይ አባታችን ተክለ ሃይማኖት ሕይወታቸዉን ሙሉ ለእግዚአብሔር በመስጠት፣ እንደ በሬ ተጠምደው፣ እንደገበሬ ታጥቀው ይህንን ዓለም ንቀው በጾም በጸሎት ተወስነው በብሕትውና ከመኖራቸው በተጨማሪ እንደቅዱሳን ሐዋርያት ወንጌልን በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ የሰበኩ፣ በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ድውያነ ሥጋን በተአምራት፣ ድውያነ ነፍስን በትምህርት የፈወሱ ሐዋርያ ናቸው፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከሚታወሱባቸው በዓላት መካከልም ታኅሣሥ ፳፬ ቀን የሚከብረው በዓለ ልደታቸው አንደኛው ነው፡፡ መጽሐፈ ስንክሳር ዜና ልደታቸውን ሲናገር ‹‹ብፁዕ ወቅዱስ ሐዲስ ሐዋርያ›› በማለት በክብር ጠርቷቸዋል፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ ‹‹እናንተን የሚቀበል እኔን ይቀበላል፤ እኔንም የሚቀበል የላከኝን ይቀበላል፡፡ ነቢይን በነቢይ ስም የሚቀበል የነቢይን ዋጋ ያገኛል፡፡ ጻድቅንም በጻድቅ ስም የሚቀበል የጻድቁን ዋጋ ያገኛል፡፡ ማንም ከእነዚህ ከተናናሾቹ ለአንዱ ቀዝቃዛ ጽዋ ብቻ በደቀ መዝሙር ስም የሚያጠጣ እውነት እላችኋለሁ፤ ዋጋው አይጠፋበትም፤›› /ማቴ.፲፥፵-፵፪/ በማለት የተናገረውን መለኮታዊ ቃል ኪዳን ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን መሠረት አድርጋ መጋቢት ፳፬ ቀን ፅንሰታቸውን፤ ታኅሣሥ ፳፬ ቀን ልደታቸውን፤ ጥር ፳፬ ቀን ስባረ ዐፅማቸውን፤ ግንቦት ፲፪ ቀን ፍልሰተ ዐፅማቸውን፣ ነሐሴ ፳፬ ቀን ደግሞ ዕለተ ዕረፍታቸውን በመንፈሳዊ ሥርዓት በደስታ ታከብራለች፡፡

የአቡነ ተክለ ሃይማኖትና የኹሉም ጻድቃን ጸሎትና በረከት ረድኤትና ምልጃ በመላው ሕዝበ ክርስቲያን ላይ ለዘለዓለሙ ጸንቶ ይኑር፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡-

መለከት መጽሔት ፲፰ኛ ዓመት፣ ቍጥር ፱፡፡

መጽሐፈ ስንክሳር (ታኅሣሥ ፳፬፣ ጥር ፳፬፣ መጋቢት ፳፬፣ ግንቦት ፲፪ እና ነሐሴ ፳፬ ቀን)፡፡

ገድለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት፡፡

ሠለስቱ ደቂቅን ከእሳት ያዳናቸው መልአክ ማን ነው? – ክፍል ሦስት (የመጨረሻ ክፍል)

 በዲያቆን ብርሃኑ አድማስ

ታኅሣሥ ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ሙት ላነሣውና ብዙ ተአምራትን ላደረገው ቅዱስ ጴጥሮስ አሁን ግን ይህን ዅሉ ጥበቃ የሚያደርግለት መልአኩ ነው፡፡ ይህ መልአክ የቅዱስ ጴጥሮስ ጠባቂ መልአክ እንደ ኾነ ብዙ ሊቃውንት በትርጓሜአቸው አስተምረዋል፡፡ በዚሁ ታሪክ ላይም፡- ‹‹ጴጥሮስም የደጁን መዝጊያ ባንኳኳ ጊዜ ሮዴ የሚሉአት አንዲት ገረድ ትሰማ ዘንድ ቀረበች፤  የጴጥሮስ ድምፅ መኾኑንም ባወቀች ጊዜ ከደስታዋ የተነሣ ደጁን አልከፈተችም፤ ነገር ግን ወደ ውስጥ ሮጣ ጴጥሮስ በደጅ ፊት ቆሞ እንዳለ አወራች። እነርሱም፦ ‹አብደሻል› አሏት። እርስዋ ግን እንዲሁ እንደ ኾነ ታስረግጥ ነበር። እነርሱም፦ ‹መልአኩ ነው› አሉ፤›› ተብሎ ተጠቅሷል /ቍ.፲፫-፲፭/፡፡ ከቤት ውስጥ የነበሩትም ‹‹ጴጥሮስ አይኾንም፤ መልአኩ ነው›› ያሏት ‹‹እርሱን ሊመስልሽ የሚችለው ጠባቂ መልአኩ ነው›› ማለታቸው ነበር፡፡ ይህም የኾነው በጥንት ክርስቲያኖች ዘንድ የጠባቂ መላእክት ጥበቃና መገለጥ በሰፊው ይታወቅ ስለ ነበረ ነው፡፡ በመጽሐፈ ጦቢት ላይም ቅዱስ ሩፋኤል ሰው መስሎ ለጦብያና ለቤተሰበው እንደዚሁም ለራጉኤልና ለቤተሰቡ ቀድሞ ጸሎታቸውን በማሳረግ፣ በኋላም ከፈተናቸው በማዳንና ሕይወታቸውን በመባረክ ተገልጦ አይተነዋል፡፡

እነዚህ ሁለት ታሪኮች የሚያስረዱን ጠባቂ መላእክት በድኅነታችን ውስጥ ትልቅ ስፋራ የሚሰጣቸውና በእርግጥም እነርሱ የሌሉበት ድኅነት የሌለ መኾኑን ነው፤ ልዩነቱ በአንዳንዶቹ ታሪኮች ላይ መገለጣቸው፣ በአንዳንዶቹ ላይ ደግሞ ተገልጠው ለሰው አለመታየታቸው ብቻ ነው፡፡ ጌታችንም በወንጌል ‹‹ከእነዚህ ከታናናሾቹ አንዱን እንዳትንቁ ተጠንቀቁ፤ መላእክቶቻቸው ዘወትር በሰማያት ያለውን የአባቴን ፊት ያያሉ እላችኋለሁና፤›› በማለት የተናገረው ስለ ጠባቂ መላእክቶቻችን ነው /ማቴ.፲፰፥፲/፡፡ በእያንዳንዱ እንቅስቃሴአችንና ፈተናችን ላይ ወደ እግዚአብሔር እያመለከቱ የሚጠብቁን፣ የሚያድኑን፣ የሚያስፈርዱልን ወይም የሚያስፈርዱብንም እነርሱ (ቅዱሳን መላእክት) ናቸውና፡፡ እንደናቡከደነፆር ያለውን አስፈርደውበት አውሬ አድርገው ሣር ያስግጡታል፡፡ እርሱ ራሱም ‹‹አንድ ቅዱስ ጠባቂ ከሰማይ ሲወርድ አየሁ፤›› ብሎ አሁንም እውነቱን አረጋግጧል /ዳን.፬፥፲፫/፡፡ እንደ ሄሮድስ ያለውን ደግሞ ‹‹ለእግዚአብሔርም ክብር ስላልሰጠ ያን ጊዜ የጌታ መልአክ መታው፤ በትልም ተበልቶ ሞተ፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈው /ሐዋ.፲፪፥፳፫/፣ በእግዚአብሔር አስፈርደው ይቀሥፉታል፡፡

እንደ ዳንኤል፣ ቅዱስ ጴጥሮስ፣ ጻድቁ ዮሴፍ፣ ሠለስቱ ደቂቅ ያሉትን ደግሞ በጠባቂነታቸው ያድኗቸዋል፡፡ ‹‹… እርሱ ከአዳኝ ወጥመድ፣ ከሚያስደነግጥም ነገር ያድንሃልና። በላባዎቹ ይጋርድሃል፤ በክንፎቹም በታች ትተማመናለህ፡፡ እውነት እንደ ጋሻ ይከብሃል። ከሌሊት ግርማ፣ በቀን ከሚበርር ፍላጻ፣ በጨለማ ከሚሔድ ክፉ ነገር፣ ከአደጋና ከቀትር ጋኔን አትፈራም። በአጠገብህ ሺሕ በቀኝህም ዐሥር ሺሕ ይወድቃሉ፤ ወደ አንተ ግን አይቀርቡም። በዓይኖችህ ብቻ ትመለከታለህ፤ የኀጥአንንም ብድራት ታያለህ። አቤቱ አንተ ተስፋዬ ነህና ልዑልን መጠጊያህ አደረግህ። ክፉ ነገር ወደ አንተ አይቀርብም፤ መቅሠፍትም ወደ ቤትህ አይገባም። በመንገድህ ዅሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዝዛቸዋልና፤ እግርህም በድንጋይ እንዳትሰናከል በእጆቻቸው ያነሡሃል … ›› ተብሎ ተጽፏልና /መዝ.፺፥፩-፲፪/፡፡

ሠለስቱ ደቂቅንም ጠባቂ መላእክቶቻቸው የሚያድኗቸው ቢኾንም ‹‹ለናቡከደነፆር የታየው አንድ  መልአክ ኾኖ ሳለ ሦስቱ መላእክት እንዳዳኗቸው ተደርጎ ለምን ይገለጻል?›› የሚል ጥያቄ ልናነሣ እንችላለን፡፡ እንዲህ ያሉትን ምሥጢራት መረዳት የምንችለው በቅዱሳት መጻሕፍት ያሉትን ተመሳሳይ ታሪኮችና ይህ የሚኾንበትን ምክንያት ስናውቅ ነው፡፡ ለምሳሌ ያህል የጌታችንን ትንሣኤ አራቱም ወንጌላውያን መዝግበውልናል፤ አራቱም የመዘገቡበት መንገድ ተቃርኖ ባይኖረውም ልዩነት ግን አለው፡፡ ዐበይት ልዩነቶቹም ሦስት ነገሮች ላይ ይስተዋላሉ፤ ይኸውም የተገለጹት መላእክት፣ ወደ መቃብሩ የመጡት ሴቶች ማንነት እና ሴቶቹ የመጡበት ሰዓት በአዘጋገብ ይለያያል፡፡ ለርእሰ ጉዳያችን ቅርበት ባለው ትምህርት ላይ ትኩረት አድርገን ጥቂት ምሳሌዎችን እንደሚከተለው እናቀርባለን፤

ቅዱስ ማቴዎስ፡- ‹‹እነሆም የጌታ መልአክ ከሰማይ ስለ ወረደ ታላቅ የምድር መናወጥ ኾነ፤ ቀርቦም ድንጋዩን አንከባሎ በላዩ ተቀመጠ። መልኩም እንደ መብረቅ ልብሱም እንደ በረዶ ነጭ ነበረ። ጠባቆቹም እርሱን ከመፍራት የተነሣ ተናወጡ እንደ ሞቱም ኾኑ። መልአኩም መልሶ ሴቶቹን አላቸው፤ ‹እናንተስ አትፍሩ፤ የተሰቀለውን ኢየሱስን እንድትሹ አውቃለሁና፡፡ እንደ ተናገረ ተነሥቶአልና በዚህ የለም፡፡› የተኛበትን ስፍራ ኑና እዩ። ፈጥናችሁምዱና ከሙታን ተነሣ፤ እነሆም ወደ ገሊላ ይቀድማችኋል፡፡ በዚያም ታዩታላችሁ፤› ብላችሁ ለደቀ መዛሙርቱ ንገሯቸው፤›› ሲል የገለጸውን /ማቴ.፳፰፥፪-፯/፣ ቅዱስ ማርቆስ፡- ‹‹ወደ መቃብሩም ገብተው ነጭ ልብስ የተጐናጸፈልማሳ በቀኝ በኩል ተቀምጦ አዩና ደነገጡ …›› በማለት መዝግቦታል /ማር.፲፮፥፭/፡፡ ቅዱስ ሉቃስ ደግሞ ‹‹እነርሱም በዚህ ሲያመነቱ እነሆ ሁለት ሰዎች የሚያንጸባርቅ ልብስ ለብሰው ወደ እነርሱ ቀረቡ ፤›› ብሎ ጽፎታል /ሉቃ.፳፬፥፬/፡፡

ቅዱስ ዮሐንስም ስለ ትንሣኤው ብዙ ነገር ካተተ በኋላ ‹‹ማርያም ግን እያለቀሰች ከመቃብሩ በስተ ውጭ ቆማ ነበር። ስታለቅስም ወደ መቃብር ዝቅ ብላ ተመለከተች፤ ሁለት መላእክትም ነጭ ልብስ ለብሰው የኢየሱስ ሥጋ ተኝቶበት በነበረው አንዱ በራስጌ ሌላውም በእግርጌ ተቀምጠው አየች፤›› ሲል መዝግቦልናል /ዮሐ.፳፥፲፩-፲፪/፡፡ እነዚህን አገላለጾች ስናያቸው የአዘጋገብ ልዩነት ቢታይባቸውም ተቃርኖና የእውነታ ልዩነት ግን የላቸውም፡፡ ቅዱስ ማቴዎስና ቅዱስ ማርቆስ ስለ አንድ መልአክ ሴቶችን ማነጋገር ቢገልጹም ሌላ መልአክ እንዳልነበረ ግን አላመለከቱም፡፡ ወንጌላውያኑ ስለ አንድ መልአክ መታየት ይመዝግቡልን እንጂ የተናገሩት ግን ስለ ተለያዩ መላእክት ነው፡፡ ቅዱስ ማቴዎስ ከመቃብሩ ወጭ ድንጋዩን አንከባሎ ስለ ተቀመጠው መልአክ ዘግቦ ከመቃብሩ ውስጥ በቀኝ በኩል (በራስጌ ወይም በግርጌ) ስላለው መልአክ አልመዘገበም፡፡ ቅዱስ ማርቆስ ደግሞ ወደ ውስጥ ከገቡ በኋላ ስላለው መልአክ መዝግቦ ከውጭ በኩል ስላለው ወይም የመቃብሩ ድንጋይ ላይ ስላለው መልአክ አልመዘገበም፡፡ ሁለቱም ግን ‹‹ሌላ መልአክ አልነበረም›› በሚያሰኝ መንገድም አልገለጹልንም፡፡

ቅዱስ ሉቃስና ቅዱስ ዮሐንስ ደግሞ ሁለቱም መላእክት መኖራቸውንና በግርጌና በራስጌ መኾናቸውን ገልጸውልናል፡፡ ስለዚህ ዅሉም ትክክል ናቸው ማለት ነው፡፡ የተለያዩና የማይቃረኑ የተባለውም ስለዚህ ነው፡፡ የተለያዩትስ ለምንድን ነው ስንል ደግሞ አንድ መሠረታዊ መልእክት እናገኛለን፤ ይኸውም ስለ መላእክቱ የተለያየ ዓይነት መገለጥ የገለጹት ለተለያዩ ሰዎች በትንንሽ የጊዜ ልዩነት የታየውን መገለጥና ለአንዳንዶችም በተቀራራቢ፣ ነገር ግን በተለያየ ጊዜ የተገለጠውን ስለ መዘገቡ ነው፡፡ ለምሳሌ ቅዱስ ዮሐንስ ለመግደላዊት ማርያም የተደረገውን የአንድ ጊዜ መገለጥ ብቻ ሲነግረን፣ ቅዱስ ሉቃስ ደግሞ ለሌሎች ሴቶች የተደረገውን (ምክንያቱም ተመላልሰው ያዩም አንድ ጊዜም ያዩ አሉ፤ እንደዚሁም ብዙ ታሪኮች በውስጡ አሉና) እያሉ ከነሰዓቱ ስለ መዘገቡ እንጂ አንዱን ነጠላ ድርጊት ለያይተውና አሳሰተው መዝግበውት አይደለም፡፡ በዚህ መሠረት በዚህ ጽሑፍ መጀመሪያ ክፍል ላይ እንዳየነው ከመንፈስ ቅዱስ መገለጥ ተሰጥቷቸውና በጊዜው የነበረውን እውነተኛውን ትውፊት ከሐዋርያትና ከነበሩት ቅዱሳን ተምረው ከተረጐሙት መምህራን ሳይረዳ ልክ እንደነዚያ ርኩሳን እንደ ተባሉት እንስሳት ሳያመሰኳ ወይም እውነታውን ሳይቆነጥጥ ወይም እንደ ዓሣዎቹ ሐዋርያት የእምነት መከላከያ ቅርፊት (ጋሻ) እና ምሥጢራትን የሚረዳበት ክንፈ ጸጋ ሳይኖረው በአመክንዮ (ሎጂክ) ብቻ እረዳለሁም፣ አስረዳለሁም ቢል ይሳሳታል፡፡

ስለዚህ የሠለስቱ ደቂቅ ድኅነትን በተመለከተ በድርሳነ ሚካኤል ላይ ሚካኤል፤ በድርሳነ ገብርኤል ላይ ገብርኤል፤  በድርሳነ ሩፋኤል ላይ ደግሞ ሩፋኤል አዳናቸው ተብሎ መገለጹ ከላይ በወንጌል እንዳየነው ትውፊቱን ለያይቶ መዘገብ እንጂ ተቃራኒ ነገር አይደለም፡፡ በዚሁ መሠረት ሦስቱን ሕፃናት አናንያ፣ አዛርያና ሚሳኤልንም ያዳኗቸው ጠባቂ መላእክቶቻቸው፤ እነዚህም ቅዱስ ሚካኤል፣ ቅዱስ ገብርኤልና ቅዱስ ሩፋኤል ናቸው፡፡ ልክ ሥላሴ ለአብርሃም በተገለጹለት መንገድ ሦስት ኾነው ከሦስቱ በስተጀርባ ቆመው መታየት ነበረባቸው ካላልን በስተቀር ከጥንት ጊዜ ጀምሮ በተላለፈው ትውፊት ሦስቱ መላእክት የሦስቱ ሕፃናት ጠባቂ መላእክት ነበሩ፡፡ እንኳን ሰዎቹ ሦስት ኾነው ይቅርና አንድም ሰው ቢኾን ሦስትና ከዚያ በላይ መላእክት ሊገኙ ይችላሉ፡፡

ዮናታን ወልደ ሳዖል ‹‹በብዙ ወይም በጥቂት ማዳን እግዚአብሔርን አያስቸግረውምና፤›› እንዳለው /፩ኛሳሙ.፲፬፥፮/፣ በአንድም በብዙም መንገድ ማዳን የእግዚአብሔር ፈቃድና ምሥጢር እንጂ የመላእክቱ የማነስና የመብዛት ጉዳይ የሚከራክር አይደለም፡፡ እንዲህ ያለው ነገር እንኳን በመላእክት ዘንድ ቃል ኪዳን ተቀብለው በሚያማልዱ፣ በሚያድኑ ሰማዕታትና ቅዱሳንም ታሪክ ላይ በተደጋጋሚ የተገለጸ መኾኑን ከተለያዩ ገድላት ለመረዳት ይቻላል፡፡ ለምሳሌ አንድ ዓሣ አስጋሪ ሰው ‹‹መርምሕናም እርዳኝ?›› እያለ ቅዱስ መርምሕናምን ሲማጸን ቅዱስ ጊዮርጊስና ቅዱስ መርምሕናም በአንድነት መጥተው ዓሣ አስጋሪውን እንደ ረዱት ‹‹ወበጊዜሃ መጽኡ ኅቡረ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወቅዱስ መርምሕናም ተጽዒኖሙ ዲበ አፍራሲሆሙ ….›› ተብሎ በተአምረ ጊዮርጊስ ተጽፎ ይገኛል፡፡ ይህ ግን በዋናነት ሊገለጽ የሚችለው በገድለ መርምሕናም እንደ ኾነ የታወቀ ነው፡፡ ስለዚህ በቅዱሳን ዘንድ አንዱ ብቻ ነው እንጂ ሌሎቹ የሉም የሚያስብል ታሪክም ድርጊትም የለም፤ ሊኖርም አይችልም፡፡ ልዩነት ያለ የሚመስለን መገለጦችን የምንረዳበት ሒደት አነስተኛ ሲኾን ብቻ ነው፡፡

የዚህ ጽሑፍየዚህ ጽሑፍ ማጠቃለያም፡- ‹‹ይህ ከኾነ ታዲያ በሠለስቱ ደቂቅ የድኅነት ታሪክ ውስጥ ቅዱስ ገብርኤል ጐልቶ ለምን ይወጣል? ዕለቱ (ታኅሣሥ ፲፱ ቀን) በዓል ኾኖ የሚከበረው ለቅዱስ ገብርኤል፤ በሥዕልም ላይ ‹አራተኛው ሰው› ተብሎ በናቡከደነፆር የተገለጸው የቅዱስ ገብርኤል ሥዕል የሚሣለው ለምንድን ነው?›› ለሚለው የብዙዎቹ ጥያቄ ምላሽ የሚሰጥ ይኾናል፡፡

ይህ የኾነበት ምክንያት ዝም ብሎ ወይም በአጋጣሚ አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ሥጋዌውን አስቀድሞ የገለጸው መላእክትንም በሰው አምሳል እንዲገለጹ በማድረግም ጭምር ነው፡፡ ለምሳሌ ለሙሴ መጀመሪያ የተገለጠለት በዚሁ መንገድ ነበረ፡፡ ‹‹የእግዚአብሔርም መልአክ በእሳት ነበልባል በእሾኽ ቍጥቋጦ መካከል ታየው፤ እነሆም ቍጥቋጦው በእሳት ሲነድ፣ ቍጥቋጦውም ሳይቃጠል አየ፤›› ተብሎ ተጽፏልና /ዘፀ.፫፥፪/፡፡ ይህም ነገረ ተዋሕዶን ወይም ምሥጢረ ሥጋዌን የሚያስረዳ መገለጥ ነው፡፡ እግዚአብሔር ራሱን በመላእክት አምሳል ሲገልጥ ደግሞ ቅድሚያውን ስፍራ የሚይዘው ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡ ምክንያቱም ገብርኤል ማለት ‹‹ቃለ እግዚአብሔር›› እንደዚሁም ‹‹ሰውና አምላክ›› ማለት ስለ ኾነ ነው፡፡ እመቤታችንን ሊያበሥር የተላከውም በዚሁ ምክንያት ነው፡፡ ስለዚህ ‹‹አራተኛ ሰው አያለሁ›› እስኪል ድረስ እግዚአብሔር ለናቡከደነፆር ሥጋዌውን (ሰው መኾኑን) ገልጦ ያሳየው ከሦስቱ ሊቃነ መላእክት መካከል ይህን የተዋሕዶ ምሥጢር በስሙም በተልእኮውም ቅዱስ ገብርኤል የተሸከመው በመኾኑ ነው፡፡

ስለዚህም ሦስቱም ሊቃነ መላእክት በጠባቂ መላእክትነታቸውና ረቂቃን ኃይላት በመኾናቸው በአዳኝነት ቢጠቀሱም እግዚአብሔር ሊገልጠው ለፈለገው ታላቅ ምሥጢር ተስማሚ የኾነውን መልአክ (ራሱ ገብርኤል መኾኑ ትርጕምና መልእክት ያለው ነውና) የነገሥታትን ልጅ በሚመስል ጐልማሳ አምሳል የንጉሠ ሰማይ ወምድር የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ ምሳሌ ኾኖ እንዲገለጽለት አድርጓል፡፡ በዓሉ ለገብርኤል የተሰጠውና ሥዕሉ የእርሱ የኾነበት ምክንያትም ይኸው ምሥጢር ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ይህን የተዋሕዶ ምሥጢር መሠረት አድርጋ በዓሉ በቅዱስ ገብርኤል ስም በታላቅ ሥርዓት እንዲከበር፣ በሥዕሉም ቅዱስ ገብርኤል ጐልቶ እንዲታይ በማድረግ ነገረ ሥጋዌውንም፣ የሕፃናቱን ተጋድሎም፣ የመላእክቱን ጠባቂነትም ስትገልጽበትና ስታስረዳበት ትኖራለች፡፡ መጽሐፍ ቅዱስን በምልዓት መረዳት ያለውም በእውነተኛው የሐዋርያትና የሊቃውንት ትምህርት ትውፊትና ሥርዓተ አምልኮ ጸንታ በምትኖረው በዚህች ቅድስት ተዋሕዶ ሃይማኖት ነው፡፡

የእግዚአብሔር ቸርነት፤ የንጽሕት ቅድስት ድንግል ማርያም ልዩ አማላጅነት፣ የሊቃነ መላእክቱ ጥበቃና የቅዱሳን ዅሉ ምልጃ አይለየን፤ አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡