ዘመነ ክረምት – ክፍል ስምንት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መስከረም ፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

፮. ዘመነ ፍሬ

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ተከታታዮች! በክፍል ሰባት ዝግጅታችን አምስተኛውን የክረምት ንዑስ ክፍል (ቅዱስ ዮሐንስን) የሚመለከት ትምህርት ማቅረባችን ይታወሳል፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን ደግሞ ስድስተኛውን ክፍለ ክረምት (ዘመነ ፍሬን) የሚመለከት ትምህርት ይዘን ቀርበናል፡፡ እንድትከታተሉን መንፈሳዊ ግብዣችንን አስቀድመናል፡፡ መልካም የንባብ ጊዜ ይኹንላችሁ!

ከመስከረም ፱ – ፲፭ ቀን ያለው ስድስተኛው ክፍለ ክረምት ‹ፍሬ› ይባላል፡፡ ‹ዘመነ ፍሬ› ደግሞ ‹የፍሬ ወቅት፣ የፍሬ ዘመን፣ የፍሬ ጊዜ› ማለት ሲኾን ይኸውም ልዩ ልዩ አዝርዕት በቅለው፣ አድገው፣ አብበው ለፍሬ የሚደርሱበት፤ የሰው ልጅ፣ እንስሳትና አራዊትም ጭምር የዕፀዋቱን ፍሬ (እሸት) የሚመገቡበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ወቅት በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚቀርቡ ምንባባትና ትምህርቶችም ይህንኑ ምሥጢር የሚዳስሱ ናቸው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ምድርን ከፈጠረ በኋላ በጥፍር የሚላጡትን (ሎሚ፣ ሙዝ፣ ትርንጎ፣ ወዘተ)፤ በማጭድ የሚታጨዱትን (ስንዴ፣ ጤፍ፣ ገብስ፣ ወዘተ)፤ በምሳር የሚቈረጡትን (ወይራ፣ ዋርካ፣ ዋንዛ፣ ዝግባ፣ ወዘተ)፤ የገነት ዕፀዋትን ፈጥሯል፡፡ እነዚህም በራሳቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ስንዴ፣ገብስ፣ ጤፍ፣ ወዘተ)፤ በጎድናቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ማሽላ፣ በቆሎ፣ ባቄላ፣ ወዘተ)፤ በውስጣቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ዱባ፣ ቅል፣ ወዘተ)፤ በሥራቸው የሚያፈሩ (ምሳሌ፡- ሽንኩርት፣ ቀይ ሥር፣ ካሮት፣ ድንች፣ ወዘተ) ተብለው በአራት ይመደባሉ (ምንጭ፡- ትርጓሜ ኦሪት ዘፍጥረት ፩፥፮-፲፫)፡፡

ተፈጥሯቸውም እንደ ሰው ከአራቱ ባሕርያት ነው፡፡ ከነፋስ በመፈጠራቸው በነፋስ ያብባሉ፤ ያፈራሉ፡፡ ከእሳት በመፈጠራቸው እርስበርሳቸው ሲፋተጉ እሳት ያስገኛሉ (አንዳንዶቹ)፡፡ ከውኃ በመፈጠራቸው ፈሳሽ ያወጣሉ፡፡ ከአፈር በመፈጠራቸው ሲቈረጡ በስብሰው ወደ አፈርነት ይቀየራሉ፡፡ እኛ የሰው ልጆችም በተፈጥሯችን (በባሕርያችን) ከዕፀዋት ጋር እንመሳሰላለን፡፡ በነፋስ ባሕርያችን ፍጥነት፤ በእሳት ባሕርያችን ቍጣ፤ በውኃ ባሕርያችን መረጋጋት፤ በመሬት ባሕርያችን ትዕግሥት ወይም ሞት ይስማማናልና፡፡ በሌላ በኩል የአዘርዕት ከበሰበሱ በኋላ መብቀልና ማፍራት የትንሣኤ ሙታን ምሳሌ ነው፡፡ አዝርዕት ከበሰበሱ በኋላ ፍሬ እንደሚያስገኙ ዅሉ ሰውም ከሞተ በኋላ ተነሥቶ እንደ ሥራው መጠን ዋጋውን ይቀበላልና፡፡ ይህንን ቅዱስ ጳውሎስ በምሳሌ አስተምሮናል፡፡ እንዲህ ሲል፤ ‹‹… የሙታን ትንሣኤ ደግሞ እንዲሁ ነው፡፡ በመበስበስ ይዘራል፤ ባለ መበስበስ ይነሣል፡፡ በውርደት ይዘራል፤ በክብር ይነሣል፡፡ በድካም ይዘራል፤ በኃይል ይነሣል፡፡ ፍጥረታዊ አካል ይዘራል፤ መንፈሳዊ አካል ይነሣል …›› (፩ኛ ቆሮ. ፲፭፥፵፪-፵፬)፡፡

አዝርዕት ተዘርተው ከበሰበሱ በኋላ በቅለው፣ አብበው በራሳቸው፣ በጎድናቸው፣ በውስጣቸውና በሥራቸው እንደሚያፈሩ ዅሉ እኛም በራስ እንደ ማፍራት ፈሪሃ እግዚአብሔርን፤ በጎድን እንደ ማፍራት እርስበርስ መደጋገፍንና መተሳሰብን፤ በውስጥ እንደ ማፍራት ንጽሕናን፤ በሥር እንደ ማፍራት ትሕትናን ገንዘብ ማድረግን ከዕፀዋትና ከአዝርዕት መማር ይገባናል፡፡ እንደዚሁም ዕፀዋት ሠላሳ፣ ስድሳ፣ መቶና ከዚያ በላይ መልካም ፍሬ እንደሚያፈሩ በመልካሟ መሬት በክርስትና የተዘራን እኛ ክርስቲያኖችም ዘር የተባለውን የእግዚአብሔርን ቃል በሚገባ ተምረን ከወጣኒነት ወደ ማእከላዊነት፤ ከማእከላዊነት ወደ ፍጹምነት በሚያደርስ የጽድቅ ሥራ በመትጋት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ መፋጠን ይኖርብናል (ማቴ. ፲፫፥፳፫)፡፡

ዕፀዋት የሚሰጡት ፍሬ እንደየማፍራት ዓቅማቸው ይለያያል፤ ፍሬ የማያፈሩ፣ ጥቂት ፍሬ የሚያፈሩ፣ ብዙ ፍሬ የሚያፈሩ ዕፀዋት ይገኛሉ፡፡ እንደዚሁ ኹሉ ምእመናንም በክርስትና ሕይወታችን የሚኖረን በጎ ምግባር የአንዳችን ከአንዳችን ይለያል፡፡ ፍሬ የክርስቲያናዊ ምግባር እንደዚሁም የሰማያዊው ዋጋ ምሳሌ ነውና፡፡ በክርስትና ሕይወት ያለምንም በጎ ምግባር የምንኖር ኀጥአን ብዙዎች የመኾናችንን፤ እንደዚሁም ጥቂት በጎ ምግባር ያላቸው ምእመናን የመኖራቸውን ያህል በአንጻሩ ደግሞ በጽድቅ ላይ ጽድቅ፣ በመልካም ሥራ ላይ መልካም ሥራን የሚፈጽሙ፤ ከጽድቅ ሥራ ባሻገር በትሩፋት ተግባር ዘወትር ጸንተው የሚኖሩ አባቶችና እናቶችም ጥቂቶች አይደሉም፡፡ ይህን ዓይነት የክርስቲያናዊ ሕይወት ልዩነት ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹በጥቂት የሚዘራ በጥቂት ደግሞ ያጭዳል፤ በበረከትም የሚዘራ በበረከት ደግሞ ያጭዳል … ለዘሪ ዘርን ለመብላትም እንጀራን በብዙ የሚሰጥ እርሱም የምትዘሩትን ዘር ይሰጣችኋል፤ ያበረክትላችሁማል፡፡ የጽድቃችሁንም ፍሬ ያሳድጋል›› በማለት ይገልጸዋል (፪ኛ ቆሮ. ፱፥፮-፲)፡፡ ገበሬ በዘራው መጠን ሰብሉን እንዲሰበስብ ‹‹ለዂሉም እንደየሥራው ዋጋውን ትከፍለዋለህ›› ተብሎ እንደ ተጻፈው ክርስቲያንም በሠራው መጠን ዋጋውን ያገኛልና በጸጋ ላይ ጸጋን፣ በበረከት ላይ በረከትን ከእግዚአብሔር ዘንድ ይጨመርልን ዘንድ ዂላችንም መልካም ሥራን በብዛት ልንፈጽም ይገባናል፡፡ ‹‹… እንግዲህ ወንድሞች ሆይ ጌታ እስኪመጣ ድረስ ታገሡ፡፡ እነሆ ገበሬው የፊተኛውንና የኋለኛውን ዝናብ እስኪቀበል ድረስ እርሱን እየታገሠ የከበረውን የመሬት ፍሬ ይጠብቃል፡፡ እናንተ ደግሞ ታገሡ፤ ልባችሁንም አጽኑ፡፡ የጌታ መምጣት ቀርቧልና›› እንዳለን ሐዋርያው (ያዕ. ፭፥፯-፰)፡፡

ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ‹‹ምድርኒ ወሀበት ፍሬሃ፤ ምድርም ፍሬዋን ሰጠች›› (መዝ. ፷፮፥፮፤ ፹፬፥፲፪) የሚለውን የዳዊት መዝሙርና ሌሎችንም ተመሳሳይ ኃይለ ቃላት ሲተረጕሙ ምድር በኢየሩሳሌም፣ በቤተ ክርስቲያን፣ በምእመናን፣ በእመቤታችን፤ ፍሬ ደግሞ በቃለ እግዚአብሔር (በሕገ እግዚአብሔር)፣ በአምልኮተ እግዚአብሔር፣ እንደዚሁም በጌታችን አምላካችን መድኂታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሚመሰል ያስተምራሉ፡፡ በዚህ መሠረት ‹‹ምድርኒ ወሀበት ፍሬሃ፤ ምድርም ፍሬዋን ሰጠች›› በሚለው ኃይለ ቃል ምድር የተባለች ኢየሩሳሌም የዘሩባትን እንደምታበቅል፤ የተከሉባትን እንደምታጸድቅ፤ አንድም ይህቺ ዓለም ፍሬን፣ አምልኮተ እግዚአብሔርን እንደምታቀርብ፤ ቤተ ክርስቲያን ወይም ምእመናን እግዚአብሔርን ሲያመልኩ እንደሚኖሩ፤ ከዚሁ ዂሉ ጋርም ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እንደ ተወለደ የሚያስረዳ ምሥጢር አለው፡፡ ‹‹ምድርኒ ወሀበት ፍሬሃ፤ ምድርም ፍሬዋን ሰጠች›› – ምድር ከተባለች ከቅድስት ድንግል ማርያም ፍሬ የተባለው ክርስቶስ መገኘቱን ለማጠየቅም ቅዱስ ገብርኤል በሉቃስ ወንጌል የተናገረው ቃል ማስረጃ ነው (ሉቃ. ፩፥፳፰)፡፡ እኛም የመልአኩን ቃል መሠረት አድርገን በዘወትር ጸሎታችን ‹‹ቡርክት አንቲ እምአንስት ወቡሩክ ፍሬ ከርሥኪ፤ አንቺ ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ፤ የማኅፀንሽ ፍሬም የተባረከ ነው›› እያልን ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እና ለልጇ ኢየሱስ ክርስቶስ ውዳሴ እናቀርባለን፡፡

በማቴዎስ ወንጌል ፲፫፥፩-፳፫ ተጽፎ እንደምናገኘው ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የክርስትና ሕይወትን ከዘርና ፍሬ ጋር በማመሳሰል አስተምሯል፡፡ ይኸውም አንድ ገበሬ ዘር ሲዘራ በመንገድ ዳር የወደቀው ዘር ከመብቀሉ በፊት በወፎች እንደ ተበላ፤ በጭንጫ ላይ የተጣለውም ወዲያውኑ ቢበቅልም ነገር ግን ጠንካራ ሥር ስለማይኖረው በፀሐይ ብርሃን እንደ ጠወለገ፤ በእሾኽ መካከል የወደቀው ደግሞ ሲበቅል በእሾኽ እንደ ታነቀ፤ ከዂሉም በተለየ መልኩ በመልካም መሬት ላይ የተጣለው ዘር ግን አድጎ መቶ፣ ስድሳ፣ ሠላሳ ፍሬ እንደ ሰጠ የሚያስረዳ ነው፡፡ ይህም ምሳሌ አለው፡፡ ጌታችን ለደቀ መዛሙርቱ እንደ ተረጐመው በመንገድ ዳር የተዘራው ዘር የእግዚአብሔርን ቃል ሰምቶ የማያስተውል ክርስቲያን ምሳሌ ነው፤ ሙሉ እምነት ስለማይኖረው በመከራው ጊዜ አጋንንት ይነጥቁታልና፡፡ በጭንጫ ላይ የተዘራው ደግሞ ቃሉን ሰምቶ ወዲያው በደስታ የሚቀበል፣ ነገር ግን ተግባራዊ የማያደርግ ክርስቲያን ምሳሌ ነው፡፡ ይህ ምእመን በጠንካራ እምነት ላይ የጸና አይደለምና በሃይማኖቱ ምክንያት መከራ ወይም ስደት በደረሰበት ጊዜ ፈጥኖ ይሰናከላል፡፡ በእሾኽ መካከል የተዘራውም ቃሉን የሚሰማ ነገር ግን በዚህ ዓለም ዐሳብና ባለጠግነት ተታሎ ቃሉን የማይተገብር ክርስቲያን ምሳሌ ነው፡፡

በመልካም መሬት የተዘራው ደግሞ ቃሉን ሰምቶ የሚተገብር ክርስቲያን ምሳሌ፡፡ እንደዚህ ዓይነት ምእመን በተማረው ትምህርት ጸንቶ ይኖራል፤ መልካም ሥራም ይሠራል፡፡ በመልካም መሬት የተዘራው ዘር ስለ አንዱ ፋንታ መቶ፣ ስድሳ፣ ሠላሳ እንደሚያፈራ ዅሉ በክርስቲያናዊ ግብር ጸንቶ የሚኖር ምእመንም ሥራውን በሦስት መንገድ ማለትም በወጣኒነት፣ በማእከላዊነትና በፍጹምነት ደረጃ እንደሚወጣ፤ ዋጋውንም በሥራው መጠን እንደሚያገኝ የሚያስረዳ ነው፡፡ አንድም ባለ መቶ ፍሬ የሰማዕታት፤ ባለ ስድሳ የመነኮሳት፤ ባለ ሠላሳ በሕግ ተወስነው በዓለም የሚኖሩ ምእመናን ምሳሌ ነው፡፡ በተመሳሳይ ምሥጢር ዂሉም የፍሬ መጠን በዅሉም ጾታ ምእመናን ሕይወት ውስጥ እንደሚስተዋል ሊቃውንት ይተረጕማሉ፡፡ ስለዚህም በሰማዕትነትም፣ በምንኵስናም፣ በዓለማዊ ሕይወትም ውስጥ የሚኖሩ ምእመናን መልካም ግብራቸው እጅግ የበዛ ከኾነ በባለ መቶ ፍሬ፤ መካከለኛ ከኾነ በባለ ስድሳ፤ ከዚህ ዝቅ ያለ ከኾነ ደግሞ በባለ ሠላሳ ፍሬ ይመሰላል (ምንጭ፡- ትርጓሜ ወንጌለ ማቴዎስ)፡፡

ከዚሁ ዂሉ ጋርም ዕፀዋት ለመጠለያነት የማይጠቅሙ እንደዚሁም ለምግብነት ወይም ደግሞ ለመድኀኒትነትና ለሌላም ልዩ ልዩ አገልግሎት የሚጠቅም ፍሬ የማያስገኙ ከኾነ ተቈርጠው ይጣላሉ፡፡ ምእመናንም ‹ክርስቲያን› ተብለን እየተጠራን ያለ ምንም በጎ ምግባርና መንፈሳዊ ሕይወት ከኖርን ከእግዚአብሔር መንግሥት ውጪ እንኾናለን፡፡ ከኀጢአት ካልተለየን በምድር መቅሠፍት ይታዘዝብናል፤ በሰማይም ገሃነመ እሳት ይጠብቀናል፡፡ ይህን እውነት በመረዳት ዂላችንም በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተን ልንኖር ያስፈልጋል፡፡ ‹‹… ምሣር በዛፎች ሥር ተቀምጧል፤ እንግዲህ መልካም ፍሬ የማያደርግ ዛፍ ዂሉ ይቈረጣል፤ ወደ እሳትም ይጣላል›› (ማቴ. ፫፥፲) ተብሎ እንደ ተጻፈው ፍሬ የማያፈሩ ዕፀዋት በምሣር ተቈርጠው እንዲጣሉ እኛም ያለ መልካም ሥራ ከኖርን በእግዚአብሔር ዘለዓለማዊ ፍርድ ከገነት፣ ከመንግሥተ ሰማያት እንባረራለን፡፡ ይህ ክፉ ዕጣ እንዳይደርስብን ከሃይማኖታችን ሥርዓት፣ ከቤተ ክርስቲያናችን ትምህርት ሳንወጣ የቅዱሳንን ሕይወት አብነት አድርገን ለጽድቅ ሥራ እንሽቀዳደም፡፡ ‹‹እንግዲህ እነዚህን የሚያኽሉ ምስክሮች እንደ ደመና በዙሪያችን ካሉልን እኛ ደግሞ ሸክምን ዅሉ ቶሎም የሚከበንን ኀጢአት አስወግደን የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን ተመልክተን በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ፤›› በማለት ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረን (ዕብ. ፲፪፥፩-፪)፡፡

ይቆየን

የኢትዮጵያ ዘመን አቈጣጠር

በዲያቆን ኃይለ ኢየሱስ ቢያ

መስከረም  ፮ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

የዘመን አቈጣጠር ዓመታትን፣ ወራትን፣ ሳምንታትን፣ ዕለታትን፣ ደቂቃን እና ድቁቅ ሰዓታትን በየሥፍራቸው (በየመጠናቸው) የሚገልጽ፤ የሚተነትን፤ የሚለካ የቤተ ክርስቲያን የቍጥር ትምህርት ነው፡፡ እነዚህ ዅሉ ተመርምረው፣ ተመዝነው፣ ተቈጥረው ሲያበቁ ምድብና ቀመር ተሰጥቷቸው የሚገኙበትን ውሳኔና ድንጋጌ የሚያሳውቅ የዘመን አቈጣጠር – ‹ሐሳበ ዘመን› ይባላል፡፡ ዓመታት፣ ወራት፣ ሳምንታት፣ ዕለታትና ሰዓታት የሚለኩት (የሚሠፈሩት፣ የሚቈጠሩት) በሰባቱ መሥፈሪያና በሰባቱ አዕዋዳት ነው፡፡ ሰባቱ መሥፈርታት የሚባሉትም፡- ሳድሲት፣ ኃምሲት፣ ራብዒት፣ ሣልሲት፣ ካልዒት፣ ኬክሮስ እና ዕለት ሲኾኑ ሰባቱ አዕዋዳት ደግሞ፡- ዐውደ ዕለት፣ ዐውደ ወርኅ፣ ዐውደ ዓመት፣ ዐውደ ፀሐይ፣ ዐውደ አበቅቴ፣ ዐውደ ማኅተም እና ዐውደ ቀመር ናቸው፡፡

  • ዐውደ ዕለት – ከእሑድ እስከ ቅዳሜ ያሉት ሰባቱ ዕለታት ሲኾኑ፤ አውራኅን (ወራትን) ለማስገኘት በዚህ ሲመላለሱ ይኖራሉ፡፡
  • ዐውደ ወርኅ – በፀሐይ ፴ ዕለታት፣ በጨረቃ ፳፱ ወይም ፴ ዕለታት ናቸው፤ ዓመታትን ለማስገኘት በዚህ ሲመላለሱ ይኖራሉ፡፡
  • ዐውደ ዓመት – በፀሐይ ቀን አቈጣጠር ፫፻፷፭ ቀን ከ፲፭ ኬክሮስ፤ በጨረቃ አቈጣጠር ፫፻፶፬ ቀን ከ፳፪ ኬክሮስ ነው፡፡ እነዚህ ሦስቱ በዕለት፤ አራቱ ደግሞ በዓመት ይቈጠራሉ፡፡ ዘመናትን ለማስገኘት በዚህ ሲመላለሱ ይኖራሉ፡፡
  • ዐውደ ፀሐይ – ፳፰ ዓመት ነው፤ በዚህ ዕለትና ወንጌላዊ ይገናኙበታል፡፡
  • ዐውደ አበቅቴ – ፲፱ ዓመት ነው፤ በዚህ ፀሐይና ጨረቃ ይገናኙበታል፡፡
  • ዐውደ ማኅተም – ፸፮ ዓመት ነው፤ በዚህ አበቅቴና ወንጌላዊ ይገናኙበታል፡፡
  • ዐውደ ቀመር – ፭፻፴፪ ዓመት ነው፤ በዚህ ዕለትና ወንጌላዊ፣ አበቅቴም ይገናኙበታል፡፡

የዘመናት (የጊዜያት) ክፍል እና መጠን

አንድ ዓመት በፀሐይ ፫፻፷፭ ቀን ከ፲፭ ኬክሮስ፤ በጨረቃ ፫፻፶፬ ቀን ከ፳፪ ኬክሮስ ነው፡፡ አንድ ወር በፀሐይ ፴ ዕለታት አሉት፤ በጨረቃ ፳፱ ወይም ፴ ዕለታት አሉት፡፡ አንድ ዕለት ፳፬ ሰዓት፤ አንድ ቀን ፲፪ ሰዓት፤ አንድ ሰዓት ፷ ደቂቃ ነው፡፡ አንድ ደቂቃ ፷ ካልዒት፤ አንድ ካልዒት ፩ ቅጽበት ነው፡፡ ኬክሮስ ማለት የክፍለ ዕለት ሳምንት (የዕለት ፩/፷ ወይም ፩/፳፬ኛ ሰዓት) ነው፡፡ አንድ ዕለት ፳፬ ሰዓት ወይም ፷ ኬክሮስ ነው፡፡

ክፍላተ ዓመት (የዓመት ክፍሎች)

የዓመት ክፍሎች፡- መጸው፣ በጋ፣ ፀደይ እና ክረምት ናቸው፡፡

  • ከመስከረም ፳፮ እስከ ታኅሣሥ ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ክፍለ ዓመት መጸው ይባላል፡፡ በዚህ ክፍለ ዓመት ሌሊቱ ረጅም፣ ቀኑ አጭር ነው፡፡
  • ከታኅሣሥ ፳፮ እስከ መጋቢት ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ክፍለ ዓመት በጋ ይባላል፡፡ በዚህ ክፍለ ዓመት የቀኑና የሌሊቱ ርዝመት እኩል ነው፡፡
  • ከመጋቢት ፳፮ እስከ ሰኔ ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ወቅት ፀደይ ይባላል፡፡ በዚህ ክፍለ ዓመት ቀኑ ይረዝማል፤ ሌሊቱ ያጥራል፡፡
  • ከሰኔ ፳፮ እስከ መስከረም ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ክረምት ይባላል፡፡ በዚህ ክፍለ ዓመት የቀኑና የሌሊቱ ርዝመት እኩል ነው፡፡

የዘመናት አከፋፈል በአራቱ ወንጌላውያን እና ዘመን የሚለወጥበት ሰዓት

  • ማቴዎስ ዘመኑን ከምሽቱ ፩ ሰዓት ጀምሮ በዓመቱ ከሌሊቱ ፮ ሰዓት ይፈጽማል፡፡
  • ማርቆስ ዘመኑን ከሌሊቱ ፯ ሰዓት ጀምሮ በዓመቱ ከጠዋቱ ፲፪ ሰዓት ይፈጽማል፡፡
  • ሉቃስ ዘመኑን ከጠዋቱ ፩ ሰዓት ጀምሮ በዓመቱ ከቀኑ ፮ ሰዓት (በቀትር) ይፈጽማል፡፡
  • ዮሐንስ ዘመኑን ከቀኑ ፯ ሰዓት ጀምሮ በዓመቱ ከቀትር በኋላ ከምሽቱ ፲፪ ሰዓት ይፈጽማል፡፡

የወራት፣ የሌሊትና የቀን ሥፍረ ሰዓት

  • መስከረም – ሌሊቱ ፲፪፤ መዓልቱም (ቀኑ) ፲፪ ሰዓት ነው፡፡
  • ጥቅምት – ሌሊቱ ፲፫፤ መዓልቱ ፲፩ ሰዓት ነው፡፡
  • ኅዳር – ሌሊቱ ፲፬፤ መዓልቱ ፲ ሰዓት ነው፡፡
  • ታኅሣሥ – ሌሊቱ ፲፭፤ መዓልቱ ፱ ሰዓት ነው፡፡
  • ጥር – ሌሊቱ ፲፬፤ መዓልቱ ፲ ሰዓት ነው፡፡
  • የካቲት – ሌሊቱ ፲፫፤ መዓልቱ ፲፩ ሰዓት ነው፡፡
  • መጋቢት – ሌሊቱ ፲፪፤ መዓልቱ ፲፪ ሰዓት ነው፡፡
  • ሚያዝያ – ሌሊቱ ፲፩፤ መዓልቱ ፲፫ ሰዓት ነው፡፡
  • ግንቦት – ሌሊቱ ፲፤ መዓልቱ ፲፬ ሰዓት ነው፡፡
  • ሰኔ – ሌሊቱ ፲፱፤ መዓልቱ ፲፭ ሰዓት ነው፡፡
  • ሐምሌ – ሌሊቱ ፲፤ መዓልቱ ፲፬ ሰዓት ነው፡፡
  • ነሐሴ – ሌሊቱ ፲፩፤ መዓልቱ ፲፫ ሰዓት ነው፡፡

የበዓላት እና አጽዋማት ኢየዐርግ እና ኢይወርድ (ከፍታ እና ዝቅታ)

  • ጾመ ነነዌ ከጥር ፲፯ ቀን በታች፤ ከየካቲት ፳፩ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • ዐቢይ ጾም ከየካቲት ፩ ቀን በታች፤ ከመጋቢት ፭ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • ደብረ ዘይት ከየካቲት ፳፰ ቀን በታች፤ ከሚያዝያ ፪ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • በዓለ ሆሣዕና ከመጋቢት ፲፱ ቀን በታች፤ ከሚያዝያ ፳፫ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • በዓለ ስቅለት ከመጋቢት ፳፬ ቀን በታች፤ ከሚያዝያ ፳፰ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • በዓለ ትንሣኤ ከመጋቢት ፳፮ ቀን በታች፤ ከሚያዝያ ፴ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • ርክበ ካህናት ከሚያዝያ ፳ ቀን በታች፤ ከግንቦት ፳፬ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • በዓለ ዕርገት ከግንቦት ፭ ቀን በታች፤ ከሰኔ ፲፱ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • ጾመ ሐዋርያት ከግንቦት ፲፮ ቀን በታች፤ ከሰኔ ፳ ቀን በላይ አይውልም፡፡
  • ጾመ ድኅነት ከግንቦት ፲፰ ቀን በታች፤ ከሰኔ ፳፪ ቀን በላይ አይውልም፡፡

የተውሳክ አወጣጥ

፩. የዕለት ተውሳክ

የዕለት ተውሳክ በቅዳሜ ይጀምራል፡፡ የቅዳሜ ተውሳክ ፰፤ የእሑድ ተውሳክ ፯፤ የሰኞ ተውሳክ ፮፤ የማክሰኞ ተውሳክ ፭፤ የረቡዕ ተውሳክ ፬፤ የሐሙስ ተውሳክ ፫፤ የዓርብ ተውሳክ ፪ ነው፡፡

፪. የአጽዋማትና የበዓላት ተውሳክ

የነነዌ ተውሳክ አልቦ (ባዶ)፤ የዐቢይ ጾም ተውሳክ ፲፬፤ የደብረ ዘይት ተውሳክ ፩፤ የሆሣዕና ተውሳክ ፪፤ የስቅለት ተውሳክ ፯፤ የትንሣኤ ተውሳክ ፱፤ የርክበ ካህናት ተውሳክ ፫፤ የዕርገት ተውሳክ ፲፰፤ የጰራቅሊጦስ ፳፰፤ የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ ፳፱፤ የጾመ ድኅነት ተውሳክ ፩ ነው፡፡

በዓላት እና አጽዋማት የሚውሉባቸው ዕለታት

  • ጾመ ነነዌ፣ ዐቢይ ጾም እና ጾመ ሐዋርያት – ሰኞ፡፡
  • ደብረ ዘይት፣ ሆሣዕና፣ ትንሣኤ እና ጰራቅሊጦስ – እሑድ፡፡
  • ስቅለት – ዓርብ፡፡
  • ርክበ ካህናት እና ጾመ ድኅነት – ረቡዕ፡፡
  • ዕርገት – ሐሙስ ቀን ይውላል፡፡

መጥቅዕ እና አበቅቴ

መጥቅዕ እና አበቅቴ ከየት መጣ ቢሉ፣

የመጀመሪያው – የፀሐይና የጨረቃ ቀን አቈጣጠር ልዩነት ነው፡፡ አንድ ዓመት በፀሐይ ፫፻፷፭ ቀን ከ፲፭ ኬክሮስ፤ በጨረቃ ፫፻፶፬ ቀን ከ፳፪ ኬክሮስ ነው፡፡ የሁለቱ ልዩነት (፫፻፷፭ – ፫፻፶፬ = ፲፩) አበቅቴ ይባላል፡፡

ሁለተኛው – የቅዱስ ድሜጥሮስ ሱባዔ ውጤት ነው፡፡ ቅዱስ ድሜጥሮስ በዓላትና አጽዋማት የሚውሉበት ቀን በጥንተ ዕለቱ እንዲውል ለማድረግ ይመኝ ነበርና ከሌሊቱ ፳፫ ሱባዔ፤ ከቀኑ ፯ ሱባዔ ገብቷል፡፡ ፳፫×፯ = ፻፷፩ ይኾናል፡፡ ፻፷፩ ለ፴ ሲካፈል ፭ ይደርስና ፲፩ ይተርፋል፤ ይህን ቀሪ አበቅቴ አለው፡፡ ፯ በሰባት ሲባዛ ፵፱ ይኾናል (፯×፯ = ፵፱)፡፡ ፵፱ ለ፴ ሲካፈል (፵፱÷፴) ፩ ደርሶ ፲፱ ይቀራል፤ ይህን ቀሪ መጥቅዕ አለው፡፡

ዓመተ ዓለምን፣ ወንጌላዊን፣ ዕለትን፣ ወንበርን፣ አበቅቴን፣ መጥቅዕን፣ መባጃ ሐመርን፣ አጽዋማትን እና በዓላትን ለይቶ ለማወቅ ሒሳባዊ ሰሌቱ እንዲሚከተለው ነው፤

ዓመተ ዓለምን ለማግኘት ስሌቱ ዓመተ ኵነኔ ሲደመር ዓመተ ምሕረት ሲኾን፣ ውጤቱ ዓመተ ዓለም ይባላል፡፡ ለምሳሌ ፶፭፻ + ፳፻፲ = ፸፭፻፲ (5500 + 2010 = 7510)፤ ፸፭፻፲ (7510) ዓመተ ዓለም ይባላል፡፡

ወንጌላዊን ለማግኘት ስሌቱ ዓመተ ዓለምን ለአራት ማካፈል ነው፡፡ ዓመተ ዓለሙ ለአራት ተካፍሎ ፩ ሲቀር ዘመኑ ማቴዎስ፤ ፪ ሲቀር ማርቆስ፤ ፫ ሲቀር ሉቃስ፤ ያለ ቀሪ ሲካፈል ዮሐንስ ይኾናል፡፡

ዕለቱን (ለምሳሌ መስከረም ፩ ቀንን) ለማግኘት ስሌቱ ዓመተ ዓለም ሲደመር መጠነ ራብዒት (ለአንድ ወንጌላዊ የደረሰው) ሲካፈል ለሰባት ነው፡፡ ዓመተ ዓለም እና መጠነ ራብዒት ተደምሮ ለሰባት ተካፍሎ ፩ ሲቀር ማክሰኞ፤ ፪ ሲቀር ረቡዕ፤ ፫ ሲቀር ሐሙስ፤ ፬ ሲቀር ዓርብ፤ ፭ ሲቀር ቅዳሜ፤ ፮ ሲቀር እሑድ፤ ያለ ቀሪ እኩል ሲካፈል ሰኞ ይኾናል፡፡

ተረፈ ዘመኑን (ወንበሩን) ለማግኘት ዓመተ ዓለም ለሰባት ተካፍሎ የሚገኘው ቀሪ ተረፈ ዘመን (ወንበር) ይባላል፡፡ ከቀሪው ላይ ስለ ተጀመረ ተቈጠረ፤ ስላልተፈጸመ ታተተ (ተቀነሰ) ብሎ አንድ መቀነስ ስሌቱ ሲኾን ቀሪው ወንበር ይባላል፡፡

አበቅቴን ለማግኘት ወንበር ሲባዛ በጥንተ አበቅቴ (፲፩) ሲካፈል ለ፴ ኾኖ ቀሪው አበቅቴ ይባላል፡፡ መጥቅዕን ለማግኘት ወንበር ሲባዛ በጥንተ መጥቅዕ (፲፱) ሲካፈል ለ፴ ኾኖ ቀሪው መጥቅዕ ይባላል፡፡

ከዚህ ላይ አዋጁን (መመሪያውን) እንመልከት፤ አዋጁም መጥቅዕ ከ፲፬ በላይ ከኾነ መጥቅዕ በመስከረም ይውላል፤ የመስከረም ማግስት (ሳኒታ) የካቲት ይኾናል፡፡ ፲፬ ራሱ መጥቅዕ መኾን አይችልም፡፡ መጥቅዕ ከ፲፬ በታች ከኾነ በጥቅምት ይውላል፤ የጥቅምት ማግስት (ሳኒታ) ጥር ነው፡፡ መጥቅዕ ሲደመር አበቅቴ ውጤቱ ዅልጊዜ ፴ ነው፡፡ መጥቅዕ አልቦ (ዜሮ) ሲኾን መስከረም ፴ የዋለበት የቀኑ ተውሳክ መባጃ ሐመር ይኾናል፡፡

መባጃ ሐመርን ለማግኘት የዕለት ተውሳክ ሲደመር መጥቅዕ ሲካፈል ለሠላሳ ነው (የዕለት ተውሳክ+መጥቅዕ÷፴ = መባጃ ሐመር)፡፡ ቍጥሩ ለሠላሳ መካፈል ካልቻለ እንዳለ ይወሰዳል፡፡

የአጽዋማት እና የበዓላት ተውሳክ አወጣጥ

ጾምን ለማግኘት ስሌቱ መባጃ ሐመር ሲደመር የጾም ተውሳክ ሲካፈል ለሠላሳ ነው (መባጃ ሐመር+የጾም ተውሳክ÷፴ = ጾም)፡፡ ቍጥሩ ለሠላሳ መካፈል ካልቻለ እንዳለ ይወሰዳል፡፡ በዓላትን ለማግኘት ስሌቱ መባጃ ሐመር ሲደመር የበዓል ተውሳክ ሲካፈል ለሠላሳ ነው (መባጃ ሐመር+የበዓል ተውሳክ÷፴ = በዓል)፡፡ ቍጥሩ ለሠላሳ መካፈል ካልቻለ እንዳለ ይወሰዳል፡፡ በዚህ ሒሳብ መሠረት በየዓመቱ የሚመላለሱ በዓላት እና አጽዋማት የሚዉሉበትን ቀን ማወቅ ይቻላል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ዝክረ ዐውደ ዓመት

በዶክተር ታደለ ገድሌ

መስከረም ፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

የዓለም ሕዝብ በየዓመቱ በታላቅ ደስታ ከሚያከብራቸውና ከሚዘክራቸው በዓላት መኻከል አንዱ የዘመን መለወጫ በዓል ነው፡፡ ዕለታት እየበረሩ፣ ወራት እየተቀመሩ አልፈው አዲስ ዘመን በባተ ቍጥር ሕዝብ ዅሉ ፍሥሐ ያደርጋል፡፡ ሰላምን፣ ብልጽግናን፣ ጤንነትን፣ ፍቅርን፣ … ለወዳጅ ዘመድ ይመኛል፡፡ አዲሱ ዓመት ዘመነ ሰላም፣ ዘመነ ጥጋብ … እንዲኾን መልካም ምኞቱን ይገልጻል፡፡ አዲስ የሥራ ዕቅድና ምኞትን በስሜቱ ያሠርፃል፡፡ ወደ ተግባርም ለመተርጐም ሌት ተቀን ይፋጠናል፡፡ በአገራችን ኢትዮጵያ የዘመን መለወጫ በዓል መስከረም ፩ ቀን ይከበራል፡፡ ‹‹ለመኾኑ በኢትዮጵያ መስከረም የአዲስ ዓመት መባቻ ኾኖ የተመረጠው ለምንድን ነው? በአራቱ ወንጌላውያንና በአራቱ እንስሳ (ኪሩቤል) መካከል ያለው የስያሜ ትሥሥርስ ምሥጢሩ ምንድን ነው?›› የሚሉና የመሳሰሉ ጥያቄዎች በአእምሯችን ሊመላለሱ ይችላሉ፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሊቃውንት ጉባኤ ሰብሳቢ ለነበሩት አለቃ አያሌው ታምሩ በአንድ ወቅት እነዚህን ጥያቄዎች አቅርበንላቸው (የካቲት መጽሔት፣ 15ኛ ዓመት ቍጥር 1፤ መስከረም 1984 ዓ.ም፣ ገጽ 4 – 7 እና 34)፤ ኢትዮጵያውያን አዲስ ዓመትን በመስከረም የሚያከብሩት ከኖኅ በፊትና በኋላ በተዘረጋው ስሌተ ዘመን እንደ ኾነ በማስረዳት የሚከተለውን ትምህርት ሰጥተዋል፤

የኢትዮጵያ ይዞታ መሠረተ ባሕርይ ከጥንት ጀምሮ ሃይማኖት ሲኾን በጽሑፍም በአፈ ታሪክም እየተወራረሰ የመጣ ነገር ነው፡፡ በሰው ፍልስፍና ወይም በመንግሥት ለውጥ ምክንያት የተናወጠ ነገር የለም፡፡ ለውጦች ጦርነቶችና ግጭቶች፣ በተለያዩ የመንግሥት መሪዎች ቢፈራረቁም መሠረተ እምነትን አልነኩም፡፡ የአገሪቱን ባህልና ታሪክ የሚነካ ለውጥ አልደረሰም፡፡ ነገር ግን ባለ ሥልጣናት በሹም ሽር ሲቀያየሩ በምርጫ የመንበረ መንግሥት መቀመጫ ቦታ ልውውጥም ሲደረግ መጥቷል፡፡ አዲስ ዓመት ከጥንት ከአዳም ጀምሮ የነበረ በዓል ነው፡፡ ከአዳም ጀምሮ የመጣውን የቍጥር ዘመን በጽሑፍ ያስተላለፈው ሄኖክ ነው፡፡ ይኸውም ሳምንታት በፍጥረት ከእሑድ እስከ ቅዳሜ ሰባት፣ የዕለት ሰዓት ሃያ አራት፣ የወር ቀናት ሠላሳ፣ የዓመት ቀናት ሦስት መቶ ስልሳ አራት ሲኾኑ ስልሳ አምስተኛዋ መዛወሪያ ቀን ናት፡፡ ጳጕሜን አምስት ቀን ስትኾን የሚዘለው ስድስተኛው ቀን ሠግር (የወር መባቻ) ይኾናል፡፡

የኢትዮጵያ ዘመን አቈጣጠር ከጥፋት ውኃ በፊት ሦስት ትውልዶችን አሳልፏል፡፡ እነርሱም ሄኖክ፣ ላሜህና ኖኅ ናቸው፡፡ ኖኅ የሰው ልጆች ዅሉ አባት እንደ ኾነው እንደ አዳም የሚቈጠር ከጥፋት ውኃ በመጨረሻ የተረፈ አባት ነው፡፡ ኖኅ ከአባቶቹ የተቀበለውን ጥበብ ዅሉ ለልጆቹ አስተላለፈ፡፡ ለአብነትም ዛሬ የምንጠቀምበት የኮሶ መድኃኒት የኖኅ ተረፈ ጥበብ ነው፡፡ ኖኅ በሰኔ ወር ከመርከብ በወጣ ጊዜ የበግ መሥዋዕት ሠውቶ ሰውን ከእግዚአብሔር ጋር አስታረቀ፡፡ እግዚአብሔርም ያን ጊዜ ከኖኅ ጋር አዲስ ቃል ኪዳን መሠረተ፡፡ ይኸውም የሰው ልጅ ልቡ ምንም ክፉ ቢኾንና ቅጣትም የማይቀርለት ቢኾን ጨርሶ እንደማያጠፋው ለኖኅ ቃል ገባለት፡፡ ምልክቱንም የቀስቱን ደጋን ወደራሱ፣ ገመዱን ደግሞ ወደ ሰው ልጆች አድርጐ በደመና ላይ ቀስት ስሎ አሳይቶታል፡፡ 

ጌታ ‹‹መዓልትና ሌሊት፣ በጋና ክረምት፣ ብርድና ሙቀት፣ ዘርና መከር ጊዜያቸውን ጠብቀው ሲፈራረቁ ይኖራሉ፡፡ በምድር ላይ ይህ አይቀርም›› በማለት እንደ ተናገረው በቃሉ መሠረት ክረምት ገባ፡፡ ክረምቱ ካለፈ በኋላ የዓመት መሥፈሪያ ሦስት መቶ ስልሳ አምስት ቀናት በመኾናቸው መስከረም አንድ ቀን የአዲስ ዓመት መባቻ ኾነ፡፡ አዲስ ዓመት ሥራውን ጨርሶ በሔደ ቍጥር፣ ዕለት ግን በየጊዜው እየታደሰ ይሔዳል፡፡ እስከ አዲስ ኪዳን መጀመሪያ ድረስ አበው በልዩ ልዩ ጊዜያት የተገለጹላቸውን ምልክቶች በመያዝ የየዘመናትን ብተት (መግቢያ) የእግዚአብሔርን ዙፋን ተሸካሚ በኾኑ በኪሩቤል መላእክት እያመሳሰሉ ገጸ ሰብእ፣ ገጸ ላህም (ላም) ገጸ ንሥር (አሞራ)፣ ገጸ አንበሳ እያሉ ዓመታትን ይመድቡ ነበር፡፡ ከስብከተ ሐዲስ በኋላ ግን ይህ ተሽሮ ወንጌልን በጻፉት አርድእት ስም ማቴዎስ፣ ማርቆስ፣ ሉቃስ፣ ዮሐንስ ስም ተሰየመ፡፡ ወንጌላውያኑ ወንጌልን ሲጽፉ ዕለት ተቀደም (በቅደም ተከተል) ነውና ተራቸውን ጠብቀው በየዓመቱ ይመላለሳሉ፡፡ ይህም ማለት ዘመኑ ዘመነ ምሕረት መኾኑን ለማብሠርና ድኅነት (መዳን) የሚሰበክበት ዘመን መምጣቱን ለመግለጽ ነው፡፡

በገጸ ሰብእ የተተካው ማቴዎስ ነው፡፡ ምሥጢሩም ‹‹ጌታ ከሰማይ ወረደ፤ ሰው ኾነ›› ብሎ ማስተማሩን የሚያመለክት ነው፡፡ በገጸ አንበሳ የተተካው ማርቆስ ነው፡፡ ይኸውም አሕዛብ በግብጽ (ምሥር) በላህም (በላም)፣ በጣዕዋ (ጥጃ) አምሳል ጣዖት አሠርተው ያመልኩ ስለ ነበር ያንን አምልኮ አጥፍቶ፣ ሽሮ በክርስቶስ እንዲያምኑ ስላደረገ ነው፡፡ በገጸ እንስሳ (ላህም) የተተካው ሉቃስ ነው፡፡ ምሳሌነቱም የጌታን መሥዋዕትነት ስለሚያስተምር ነው፡፡ በገጸ ንሥር የተተካው ዮሐንስ ነው፡፡ ንሥር ከአዕዋፍ ዅሉ መጥቆ ይሔዳል፡፡ መሬትም ላይ ምንም ኢ ምንት ነገር ብትወድቅ አትሠወረውም፡፡ ዓይኑ ጽሩይ (ብሩህ) ነው፡፡ ይህም ማለት ቅዱስ ዮሐንስ ዓለም ሳይፈጠር፣ ዘመን ሳይቈጠር ወደ ነበረው ኹኔታ በሕሊናው ርቆ በመሔድ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ቀዳማዊ ቃል መኾኑን፤ እግዚአብሔርም ዓለሙን የፈጠረው በእርሱ ቃል እምነት መኾኑን፤ ያም ቃል ሰው መኾኑን ስለሚያስተምር ነው ገጸ ንሥር የተባለው፡፡ የሦስቱ ወንጌላውያን ትምህርት ታሪክ ጠቀስ ኾኖ ለሰሚዎችና አንባቢዎች ዅሉ በቶሎ ሲረዳ፣ የዮሐንስ አስተምህሮ ግን ጥልቅ የአእምሮ ብስለትና ምርምርን ይጠይቃል፡፡

ዘመን በተለወጠ ቍጥር ከሰው ልጆች ስሜት ጋር አብሮ የሚንቀሳቀስ ተስፋ አለ፡፡ በጥፋት ዘመን ሰማይ በደመና ተሸፍኖ፣ ከላይ ዝናም፣ ከታች የሚፈልቀው ጎርፍ የኖኅ ሰዎችን አስጨንቋቸው ነበር፡፡ በኋላ ግን ምድር ላይ ለውጥ ታየ፡፡ ነፋስ ነፈሰ፡፡ ብርሃን ፈነጠቀ፡፡ አበባ አበበ፡፡ የኖኅ መልእክተኛ የኾነችው ርግብም ‹‹ማየ አይህ ነትገ፤ የጥፋት ውኃ ጐደለ›› እያለች ርጥብ ቄጠማ በአፏ ይዛ መጥታ ስታበሥረው የኖኅ ሰዎች ከመርከቧ ወደ መሬት ሲወርዱ በመጀመሪያ አበባ፣ እንግጫ፣ ቄጠማ፣ የለመለመ ሣር … አገኙ፡፡ እግዚአብሔርንም በአንቃዕድዎ ልቡና አመሰገኑና በዓላቸውን አከበሩ፡፡ በዚህም አምሳል ክረምት አልፎ መሬት በምታሸበርቅበት በምታብበት ከመስከረም አንድ ቀን ጀምሮ አዲስ ዓመታችንን እናከብራለን፡፡ ሰውም ከመሬት የተገኘ በመኾኑ እንደ ዕፀዋትና እንደ አበቦች ዅሉ በመስከረም ወር በተስፋ ስሜት ይለመልማል፡፡ ያጣው አገኛለሁ፣ የታመመው እድናለሁ ብሎ በቁርጥኝነት ይነሣሣል፡፡ በዘልማድም እምነቶች ይገለጻሉ፤ ‹‹በዮሐንስ እረስ፣ በማቴዎስ እፈስ … ጳጕሜ ሲወልስ ጎታህን አብስ … ጳጕሜ ሲበራ ስንዴህን ዝራ›› እያሉ ገበሬዎች ይናገራሉ፤ ይተነብያሉ፡፡ ገበሬዎች ገና በግንቦት ወር የክረምቱን አገባብ ለይተው የሚዘሩትን ዘር ደንብተው የሚያውቁ ሜትሮሎጂስቶች (የአየር ጠባይዕ ትንበያ ባለሙያዎች) ናቸው፡፡

አለቃ አያሌው እንዳስተማሩት ዐውደ ዓመት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ባሕረ ሐሳብ መሠረት የሚከበርና መንፈሳዊ ምሥጢር ያለው ሃይማኖታዊም አገራዊም በዓል ነው፡፡ በቅዱስ ዮሐንስ በዓል በቤተ ክርስቲያን ከሚፈጸመው መንፈሳዊ አገልግሎት ባሻገር በአዲሱ ዓመት ዋይዜማ በየቤቱ ጨፌና ቄጠማ ይጎዘጎዛል፡፡ አበባ በሥርዓቱ እየተዘጋጀ በየቦታው ይቀመጣል፡፡ ልጆችና አረጋውያን አዳዲስ ልብሳቸውን ለብሰው በደስታ ይፈነድቃሉ፡፡ አመሻሽ ላይ ችቦ አቀጣጥለው ‹‹ኢዮሃ አበባዬ መስከረም ጠባዬ … ኢዮሃ የበርበሬ ውኃ … በሸዋ በጎንደር፣ በትግራይ በወሎ፣ በሐረርጌ፣ በሲዳሞ … ያላችሁ እንዴት ከረማችሁ? እንኳን ከዘመን ዘመን ከጨለማ (ሰኔ፣ ሐምሌ፣ ነሐሴ) ወደ ብርሃን (መስከረም) በሰላም አሸጋገራችሁ! … እንጉሮ ገባሽ በያመቱ ያምጣሽ …›› እያሉ ያቀጣጠሉትን ችቦ በአየር ላይ እየወረወሩ ደስታቸውን ሲገልጹ፣ የምሽቱም የችቦ እሳት ርቀት እስከሚወስነው አድማስ ድረስ ከቀዬ ቀዬ፣ ከአድባር እስከ አድባር፣ ከመንደር እስከ መንደር … ሲንቀለቀልና ሲንቦገቦግ መሬት የእሳት ላንቃዋ ተከፍቶ ነበልባል የምትተፋ ትመስላለች፡፡ የአየር ላይ ወጋገኑን ሲመለከቱት ደግሞ እግዚአብሔር ከመንበረ ጸባዖቱ ወርዶ የብርሃን አክሊል ደፍቶ ቀይ መጐናጸፊያ ተጎናጽፎ ጨለማውን እየገፈፈ በጠፈር (በአየር) ላይ እየተንሳፈፈ ወደ መሬት የሚወርድባት የመጨረሻዋን የምጽአትን ቀን ታስታውሳለች – የዕንቍ ጣጣሽ ሌሊት፡፡

አባቶች የችቦ ብርሃን ላሰባሰበው ሕዝብ ቡራኬና ምርቃት ያደርጋሉ፡፡ ‹‹የተዘራውን እኽል እኽለ በረከት፣ የዘነመውን ዝናም ዝናመ ምሕረት፣ ዘመኑን የሰላም ዓመት ያድርግልን፡፡ እኽል ይታፈስ፤ ይርከስ፡፡ ሳቢ በሬውን፣ አራሽ ገበሬውን ይባረክ፣ ቁንጫ፣ ተባይ ተምች፣ አንበጣ … ፀረ ሰብል ዅሉ እንደ ችቦው ተቀጣጥለው ይንደዱ …›› እያሉ ይመርቃሉ፡፡ እናት አባት በልጆቻቸው፣ በወዳጅ ዘመዶቻቸው የተበረከተላቸውን የእንግጫ ጉንጉን በራሳቸው፣ በእንጀራ ማቡኪያና መሶቡ፣ ከቤቱ ምሰሶ ላይ … ያሥራሉ፡፡ ይህ በአበባ የተዘጋጀ የእንግጫ ጉንጉን የመስቀል ደመራ ዕለት ከእሳቱም ከዐመዱም ላይ ይጣላል፡፡ ተምሳሌቱም እንደ ቁንጫ ዅሉ ቁርጥማቱ ራስ ምታቱ፣ ምችጎንፍ ቁርጠቱ፣ ምቀኛ፣ ሸረኛ፣ ሰላቢው፣ ሌባ፣ ቀማኛ ቀጣፊው … እንዲቃጠልና እንዲጠፋ ነው፡፡ በቤቱም (በአባወራው ቤት) በረከትና ሞገስ (አግሟስ) እንዲቀርብም ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በአዲስ ዓመት አዲስ ሕይወት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መስከረም ፫ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ወንጌላዊው ዮሐንስ በራእዩ ‹‹እነሆሉን አዲስ አደርጋለሁአዲስ ሰማይንና አዲስ ምድርንም አየሁ፤ ፊተኛው ሰማይና ፊተኛይቱ ምድር አልፈዋልና፡፡ ባሕርም ወደ ፊት የለም›› በማለት እንደ ተናገረው (ራእ. ፳፩፥፩-፭) ዘመን እያለፈ አዲስ ዘመን ይተካል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን በዕድሜ ላይ ዕድሜን እየጨመረ፣ ዘመናትን እያፈራረቀ በየጊዜያቱ አዲስ ዓመትን ያመጣልናል፡፡ አሁንም በእርሱ ቸርነት ለ፳፻፲ ዓመተ ምሕረት ደርሰናል፡፡ እኛም ዘመን በመጣ ቊጥር ‹‹እንኳን በሰላም አደረሳችሁ!›› እንባባላለን፡፡ ስለ ትናንትና እንጂ ስለ ነገ ባናውቅም እስከ ዛሬ ድረስ በመቆየታችንም እንደሰታለን፡፡ ነገን በተስፋ ለሚጠባበቅ ሰው በእውነትም ዓመት አልፎ ዓመት ሲተካ በጣም ያስደስታል፡፡ ነገር ግን ያለፈውን ዓመት ስንዋሽ፣ ስንሰርቅ፣ ስንዘሙት፣ ስንጣላ፣ ስንተማማ፣ ስንደባደብ፣ ስንሰክር አሳልፈን ከኾነ ‹‹እንኳን አደረሳችሁ!›› የሚለው ቃል ርግማን ይኾንብናል፡፡

ስለ ተለወጠው ዘመን ሳይኾን ስላልተቀየረው ሰብእናችን፤ ስላልተለወጠው ማንነታችን፤ ስላልታደሰው ሥጋችን ማሰብ ይኖርብናል፡፡ በኀጢአት እየኖሩ ዐውደ ዓመትን ማክበር ራስን ያለ ለውጥ እንዲቀጥል ማበረታታት ነውና ከምንቀበለው ዘመን ይልቅ መጪውን ዘመን ለንስሐ ለማድረግ መዘጋጀት ይጠበቅብናል፡፡ ያሳለፍነውን የኀጢአት ጊዜ እያሰብን እስከ ዛሬ ድረስ የጠበቀንን እግዚአብሔርን እያመሰገንን ሕይወታችንን በጽድቅ ልናድስ ይገባናል፡፡ በንስሐ ባልታደሰ ሕይወታችን በዕድሜ ላይ ዕድሜ ቢጨመርልን ለእኛም ለዘመኑም አይበጅምና፡፡ ‹‹ባረጀ ልብስ አዲስ እራፊ የሚያኖር የለም፤ መጣፊያው ልብሱን ይቦጭቀዋልና፡፡ መቀደዱም የባሰ ይኾናል›› እንዳለ ጌታችን በወንጌል (ማቴ. ፱፥፲፯)፡፡

ያለ ክርስቲያናዊ ምግባር እየኖርን ዘመንን ብቻ የምንቈጥር ከኾነ ሕይወታችንን ከሰብአዊነት ክብር ብሎም ከክርስቲያናዊ ሕይወት በታች እናደርገዋለን፡፡ ራስን ከጊዜ ጋር ማወዳደር መቻል ክርስቲያናዊ ሓላፊነት ነው፡፡ ይኸውም ጊዜ ሳይቀድመኝ ልቅደመው ብሎ ማሰብ መቻል ነው፡፡ በአሮጌ ሕይወት ውስጥ ኾነን ዓመቱን አዲስ ከማለት ይልቅ ከኀጢአት ወደ ጽድቅ በመሸጋገር ራሳችንን በጽድቅ ሥራ ማደስ ይበልጣል፡፡ ስለዚህም ያለፈውን ዓመት በምን ኹኔታ አሳለፍሁት? በመጭው ዓመትስ ምን ማድረግ ይጠበቅብኛል? በሚል ጥያቄ መነሻነት በአዲሱ ዓመት መንፈሳዊ ዕቅድ ሊኖረን ይገባል፡፡

በመሠረቱ ዘመን ራሱን እየደገመ ይሔዳል እንጂ አዲስ ዓመት የለም፡፡ ሰዓታትም ዕለታትም እየተመላለሱ በድግግሞሽ ይመጣሉ እንጂ ከዚህ በፊት ያልነበረ ሰዓት ወይም ቀን ወይም ደግሞ ወር አለዚያም ዓመት የለም፡፡ ወርኀ መስከረምም ለብዙ ሺሕ ዓመታት ራሱን እየደገመ በየዓመቱ አዲስ ሲባል ይኖራል እንጂ ሌላ መስከረም የለም፡፡ ‹‹የኾነው ነገር እርሱ የሚኾን ነው፤ የተደረገውም ነገር እርሱ የሚደረግ ነው፡፡ ከፀሐይም በታች አዲስ ነገር የለም፡፡ ማንምእነሆ ይህ ነገር አዲስ ነውይል ዘንድ ይችላልን? እርሱ ከእኛ በፊት በነበሩት ዘመናት ተደርጎአል›› እንዳለ ጠቢቡ ሰሎሞን (መክ. ፩፥፱-፲)፡፡ ዘመን አዲስ የሚባለው እኛ ሰዎች (ክርስቲያኖች) ሕይወታችንን በጽድቅ ስናድስ ነው፡፡ ያለ መልካም ሥራ የሚመጣ ዓመት፤ ከክፉ ግብር ጋር የምንቀበለው ዘመን አዲስ ሊባልም፣ ሊኾንም አይችልም፡፡ የሰው ልጅ መንፈሳዊ ሕይወት በመልካም ሥራ ሲዳብር ግን መጭው ዘመን ብቻ ሳይኾን ያለፈው ዘመንም አዲስ ነው፡፡

በዘመናት ዑደት ውስጥ ሕይወታቸውን በሙሉ በጽድቅ የሚያሳልፉ ወይም ኀጢአታቸውን በንስሐ የሚያጸዱ ብዙ ጻድቃን ምእመናን ቢኖሩም ሰውነታችንን ጥለን በክፉ ምግባር እየኖርን  ዕድሜያችንን የምንቈጥር ኃጥኣን ጥቂቶች አይደለንም፡፡ ስለኾነም በኀጢአት ያሳለፍነውን ዘመን በማሰብ መጭውን ዘመን ለመልካም ሥነ ምግባር ልናውለው፤ አንድም ለንስሐ መግቢያ ልናደርገው ያስፈልጋል፡፡ ‹‹የአሕዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት፤ በመዳራትና በሥጋ ምኞትም፣ በስካርም፣ በዘፈንም፣ ያለ ልክም በመጠጣት፣ ነውርም ባለበት፣ በጣዖት ማምለክ የተመላለሳችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃል›› በማለት ቅዱስ ጴጥሮስ አስተምሮናልና (፩ኛ ጴጥ. ፬፥፫)፡፡ እናም ለአዲስ ዓመት አዲስ ሕይወት እንደሚያስፈልግ በመረዳት ራሳችንን በንስሐ ሳሙና አሳጥበን በንጽሕና ልንኖር ያስፈልጋል፡፡ ‹‹ታጠቡ፤ ሰውነታችሁንም አንጹ፡፡ የሥራችሁን ክፋት ከዓይኔ ፊት አስወግዱ፡፡ ክፉ ማድረግን ተዉ … ልባችሁን አንጹ፤ ሰውነታችሁንም ንጹሕ አድርጉ›› ተብለን ታዝዘናልና (ኢሳ.፩፥፲፮፤ መጽሐፈ ኪዳን)፡፡

በአጠቃላይ በዚህ አዲስ ዓመት ከክፉ ምግባር ዅሉ ተለይተን፣ ከዚህ በፊት በሠራነው ኀጢአታችን ንስሐ ገብተን፣ ለወደፊቱ በጽድቅ ሥራ ኖረን እግዚአብሔርን ልናስደስት ይገባናል፡፡ ‹‹ይደልወነ ከመ ንግበር በዓለ ዐቢየ በኵሉ ንጽሕና እስመ ይእቲ ዕለት ቅድስት ወቡርክት፡፡ ወንርኀቅ እምኵሉ ምግባራት እኩያት፡፡ ወንወጥን ምግባራተ ሠናያተ ወሐዲሳተ በዘቦቶን ይሠምር እግዚአብሔር፤ አሁንም በፍጹም ንጽሕና ታላቅ በዓልን አድርገን ልናከብር ይገባናል፡፡ ይህቺ ዕለት ከሌሎች ዕለታት ተለይታ የተባረከች ናትና፡፡ ከክፉ ሥራዎችም ተለይተን እግዚአብሔር ደስ የሚሰኝባቸውን አዳዲስ የኾኑ በጎ ሥራዎችን እንሥራ›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (መጽሐፈ ስንክሳር፣ መስከረም ፩ ቀን)፡፡

የተወደዳችሁ ምእመናን! ‹‹ዐዘቅቱ ይሙላ፤ ተራራውና ኮረብታውም ዅሉ ዝቅ ይበል፡፡ ጠማማውም የቀና መንገድ ይኹን፡፡ ሸካራውም መንገድ ትክክል ይኹን፡፡ ሥጋም የለበሰ የእግዚአብሔርን ማዳን ይይ›› ተብሎ እንደ ተነገረው (ሉቃ. ፫፥፫-፮) በኑፋቄ የጎደጎደው ሰውነታችንን በቃለ እግዚአብሔር በመሙላት፤ በትዕቢት የደነደነውን ተራራውን ልቡናችንን በትሕትና በማስገዛት፤ በክፋት የተጣመመው አእምሯችንን በቅንነት በማስጓዝ፤ በኀጢአት የሻከረውን ልቡናችንን በንስሐ በማስተካከል አዲሱን ዓመት የመልካም ምግባር ዘመን እናድርገው፡፡ በተጨማሪም ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹እንግዲህ ያለ እርሾ እንዳላችሁ አዲሱን ሊጥ ትኾኑ ዘንድ አሮጌውን እርሾ አስወግዱ›› በማለት እንዳዘዘን (፩ኛ ቆሮ.፭፥፯)፣ በኀጢአት እርሾ የተበከለውን ሰውነታችንን በጽድቅ ሕይወት እናድሰው፡፡ በአዲሱ ዓመት በክርስቲያናዊ ምግባር መኖር ከቻልን ከጊዜ ጋር የሚጣጣም አዲስ ሕይወት ይኖረናል ማለት ነው፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም የደስታችን መጠን በልክ መኾን አለበት፡፡ አሁን አሁን የበዓሉን መንፈሳዊነት የሚያጠፉ እንደ ከልክ በላይ መመገብና መመጣት፣ መስከር፣ መጨፈር፣ መጮኽ፣ ወዘተ. የመሳሰሉ የውጭ ዓለም የባህል ወረራዎች በየከተሞች ተስፋፍተዋል፡፡ እነዚህ ሰይጣናዊ ድርጊቶች ወጣቱን ትውልድ ለጥፋት የሚጋብዙ የኀጢአት መሣሪያዎች ናቸውና ለራሳችንም ለአገራችንም ህልውና ሲባል አጥብቀን ልንከላከላቸው ይገባል፡፡ አዲሱን ዓመት ለማየት እንደ ጓጉ በልዩ ልዩ ምክንያት ለመድረስ ያልታደሉትን፤ በደዌ ዳኛ በአልጋ ቁራኛ ተይዘው በየጠበሉና በየሆስፒታሉ የሚሰቃዩትን፤ በጦርነት፣ በረሃብ፣ በስደት፣ ወዘተ. በመሳሰሉ ችግሮች የሚጨነቁትን ወገኖቻችንን በማሰብና መንፈሳዊ ትውፊቱን የጠበቀ አከባበርን መሠረት በማድረግ ዓመት በዓሉን ማክበር ይጠበቅብናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በአውሮፓ የመጀመሪያው ዓለም አቀፍ የቤተ ክርስቲያን ጥናት ጉባኤ ተካሔደ

ካህናት አባቶች፣ ጥናት አቅራቢ ምሁራን፣ የዝግጅት ኮሚቴው አባላት እና የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

በአውሮፓ ማእከል

ጳጕሜን ፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማእከል የሙያ አገልግሎት እና አቅም ማጎልበቻ ክፍል አስተባባሪነት ‹‹የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅርሶች›› በሚል ርእሰ ጉዳይ የመጀመሪያው ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የጥናት ጉባኤ በስዊድን አገር በሉንድ ዩኒቨርሲቲ ከነሐሴ ፳፯ – ፳፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ተካሔደ፡፡

በጥናት ጉባኤው በታዋቂ ምሁራን በአማርኛ እና እንግሊዝኛ ቋንቋዎች በልዩ ልዩ አርእስት የተዘጋጁ የምርምር ሥራዎች የቀረቡ ሲሆን፣ ከአውሮፓ ሀገራት የመጡ በርካታ ምእመናን እና የስዊድን ዜጎች በተዳሚነት ተሳትፈዋል፡፡

በመጀመሪያው ጉባኤ በለንደን ከተማ የደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አገልጋይ የሆኑት ቀሲስ አባተ ጉበና ‹‹የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅርስ ጥቅሞች፣ የቤተ ክርስቲያን ደኖች እንደ አገር ብዝኀ ሕይወት ማሳያነት›› በሚል ርእስ ባስተላለፉት መልእክት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በደን ጥበቃ የላቀ አስተዋጽዖ ከማበርከቷ ባሻገር የብዝኀ ሕይወት መገኛ እንደ ሆነችም አስረድተዋል፡፡

በሉንድ ዩኒቨርሲቲ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር ሳሙኤል ሩቢንሰን፣ ‹‹የኢትዮጵያ ሃይማኖታዊ ቅርሶች ለክርስትና ታሪክ ያላቸው አስተዋጽዖ›› በሚል ርእስ ባቀረቡት ጥናታዊ ጽሑፍ በምዕራባውያን ጫና ምክንያት የክርስትና ታሪክ በመጀመሪያ ወደ አውሮፓ መግባቱ፤ በቅኝ ግዛት ዘመን ወደ አፍሪካ እና እስያ መስፋፋቱ በተዛባ መልኩ እንደሚነገር አውስተዋል፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ታሪክ በክርስትና ታሪክ ውስጥ የሚያካትቱ አካላትም የኢትዮጵያ ባህል ከሌሎች አገሮች ተገንጥሎ የወጣ እንደ ሆነ እና ለክርስትና ታሪክም አስተዋጽዖ እንደሌለው የማድረግ ዝንባሌ እንደሚታይባቸው ፕሮፌሰሩ አብራርተዋል፡፡ ‹‹በመጀመሪያው ምዕት ዓመት በነበረው የክርስትና አመሠራረት ላይ የኢትዮጵያን አስተዋጽዖ አለማካተት የክርስትናን ታሪክ ጎደሎ እንዲኾን ያደርዋል›› የሚሉት ፕሮፌሰር ሩቢንሰን፣ ክርስትና ከኢየሩሳሌም ወደ አውሮፓ፤ ከዚያም በቅኝ ግዛት ዘመን ወደ አፍሪካ እና እስያ ደረሰ የሚለው አስተሳሰብ ስሕተት መሆኑን በጥናታቸው ጠቁመዋል፡፡

ጥናት አቅራቢዎች

‹‹የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅርሶች ታሪክና ጥበቃ›› በሚል ርእስ ጥናት ያቀረቡት የአርኪዮሎጅ እና አንትሮፖሎጅ ምሁሩ እንግሊዛዊው ፕሮፌሰር ዴቪድ ፊልፕሰን፣ ከዘመነ አክሱም ጀምሮ ያለውን የኢትዮጵያ ቅርሶችን ታሪክ ካስታወሱ በኋላ ስለ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት አሠራር፣ ስለሚደረግላቸው ክብካቤና ጥበቃ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ በዘራፊዎች ተወስደው በውጭ አገር የሚገኙ የኢትዮጵያ ቅርሶችን ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ የሚደረገውን ጥረት እንዳይሳካ የሚያደርጉ ጉዳዮችንም ዳሰዋል፡፡ ፕሮፌሰሩ ፊሊፕሰን በእንግሊዝ አገር የሚገኙ ቅርሶች ወደ ኢትዮጵያ ይመለሱ ተብሎ እንቅስቃሴ በሚደረግበት ወቅት ቅርሶችን በማስተዳደር ላይ ያሉት የብሪታንያ ሙዚየም ባለ ሥልጣናት ‹‹ቅርሶች ወደ ኢትዮጵያ ቢመለሱ፣ ጥበቃና ክብካቤ የሚያደርግላቸው የለም›› የሚል ምክንያት እንደሚሰጡ በጥናታቸው አውስተዋል፡፡ ይሁን እንጂ ከእንግሊዝ ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱ ቅርሶችም እንዳሉ የጠቆሙት ፕሮፌሰሩ ለአብነትም በ፲፰፻፸፪ ዓ.ም የተመለሰው ክብረ ነገሥት የተባለው መጽሐፍ በአዲስ አበባ ከተማ በመርካቶ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን በጥሩ ክብካቤ እንደሚገኝ ከሰባ ዓመታት በፊት ማየታቸውን ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ተሞክሮ በመነሣትም ዅሉም ቅርሶቿ ቢመለሱላት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሥርዓት እንደምትጠብቃቸው በመጠቆም ፕሮፌሰር ፊሊፕሰን ጥናታዊ ጽሑፋቸውን አጠናቀዋል፡፡

በኖርዌይ አገር የአካባቢያዊ ኬሚስትሪ ምሁሩ ዶክተር ኪዳኔ ፋንታ በበኩላቸው ‹‹የኢትዮጵያ ክርስቲያናዊ ሥዕላት ፊዚኮ – ኬሚካዊ ምርመራ›› በሚል ርእስ ባዘጋጁት ጥናታዊ ጽሑፋቸው ሥዕላቱ የተሠሩበትን ንጥረ ነገር ማወቅ ሥዕላቱን ለመጠበቅና እና እድሳት ለማድረግ ጠቀሜታ እንዳለው አመላክተዋል፡፡ ዘመኑ ያፈራቸውን የረቀቁ የቤተ ሙከራ መሣሪያዎች በመጠቀምና ምርመራ በማድረግ ልዩ ልዩ ሥዕላት፣ የሕንጻ ዓምዶች እና የብራና ጽሑፎች የተዘጋጁበትን ንጥረ ነገር፣ ዘመን እና ቦታ ለመለየትና ለመረዳት እንደሚቻልም በምሳሌ አስረድተዋል፡፡

ሌላኛው ጽሑፍ አቅራቢ የታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር ተከሥተ ነጋሽ ደግሞ ‹‹ዋሌ ኢየሱስ፣ የአክሱም ዘመን ቤተ ክርስቲያን በዛግዌ ምድር›› በሚል ርእስ ባቀረቡት ጥናት በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ውስጥ የሚገኘውን ጥንታዊ የዋሻ ቤተ ክርስቲያንን አሠራር የሚመለከት ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ የዋሌ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን አሠራር በአክሱም ዘመን ከታነጹ አብያተ ክርስቲያናት ጋር ተመሳሳይነት እንዳለውም አስረድተዋል። በቤተ ክርስቲያኑ ዙሪያ የሚኖሩ መነኮሳትና ካህናት ቤተ ክርስቲያኑ ከላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት አስቀድሞ በስድስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን እንደ ተመሠረተ ማስረጃዎች መሆናቸውንም ፕሮፌሰር ተከሥተ ነጋሽ አውስተዋል፡፡

ነሐሴ ፳፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከቅዳሴ በኋላ በሉንድ ደብረ መዊዕ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ሁለተኛው የጥናት ጉባኤ የቀጠለ ሲኾን፣ በልዩ ልዩ አርእስት የተዘጋጁ ሦስት ጥናታዊ ጽሑፎች በአማርኛ ቋንቋ ቀርበዋል፡፡ በመጀመሪያ ‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ቅርሶች ለመጠበቅ፣ ለምእመናን ምን ያኽል ትምህርት ተሰጥቷል?›› በሚል ርእስ የታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር ሽፈራው በቀለ እስከ አሁን ድረስ በአደረጉት የሰነድ ምርመራ የቅርሶችን ምንነት እና አጠባበቅ የሚያስረዱ ጽሑፎችን ማግኘት አለማቻላቸውን፤ በቤተ ክርስቲያን የሚሰጡ አብዛኞቹ ትምህርቶችም የቅርስ አያያዝን አለማካተታቸውን አስገንዝበዋል። በዚህ የተነሣም የቤተ ክርስቲያን ቅርሶች የመጥፋት አደጋ እንደ ተጋረጠባቸው ገልጸዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ሕንጻዎችን፣ ንዋያተ ቅድሳትን እና መጻሕፍትን ለመጠበቅና ከጥፋት ለመታደግ ይረዳ ዘንድ መሠረታዊ የቅርስ ጥበቃ፣ ክብካቤ እና ጥገናን የሚመለከቱ ሥልጠናዎችን መስጠት አስፈላጊ መሆኑንም ፕሮፌሰር ሽፈራው በጥናታቸው ማጠቃለያ ጠቁመዋል፡፡

ጥናት አቅራቢዎች

በመቀጠል የፊሎሎጅ ምሁሩ ቀሲስ ዶክተር አምሳሉ ተፈራ ‹‹ጥንታዊ የብራና ላይ ጽሑፎቻችን ዘረፋ፣ የአያያዝ ጉድለትና ትኩረት የሚሹ ጉዳዮች›› በሚል ርእስ የምርምር ሥራቸውን አቅርበዋል፡፡ የብራና ጽሑፎችን ምንነት፣ ዓይነትና ይዘት በመተንተን ጥናታቸውን የጀመሩት ቀሲስ ዶ/ር አምሳሉ፣ በውጭ ሀገራት የሚገኙ በርካታ የኢትዮጵያ ቅርሶች በአብዛኛው በዘረፋ መልክ የተወሰዱ፤ የተወሰኑት ደግሞ ነገሥታቱ ለመሪዎች በስጦታ መልክ ያበረከቷቸው መሆናቸውን አውስተዋል፡፡ እንደ ቀሲስ ዶ/ር አምሳሉ ማብራሪያ በአጠቃላይ 6,245 የብራና መጻሕፍት በልዩ ልዩ መንገድ ከኢትዮጵያ የተወሰዱ ሲሆን፣ አብዛኞቹም በእንግሊዝ፣ በጀርመን፣ በጣልያን እና ቫቲካን አገሮች ይገኛሉ፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም ጥቂት የብራና ጽሑፎች በልዩ ልዩ ጊዜያት ወደ ኢትዮጵያ መመለሳቸውን አስታውሰው እርሳቸው ተሳትፎ ያደረጉበትን ከአሜሪካው ሀዋርድ ዩኒቨርሲቲ ወደ ደብረ ሊባኖስ ገዳም የተመለሰውን የገድለ ሰራባሞን እና ሌሎችም ቅርሶችን በማስረጃነት ጠቅሰዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን፣ መንግሥት እና እያንዳንዱ ግለሰብ ቅርሶችን የመጠበቅ ሓላፊነት እንዳለበት በማሳሰብ ቀሲስ ዶ/ር አምሳሉ ጥናታቸውን አጠቃለዋል፡፡

በጥናት ጉባኤው ማጠናቀቂያ ዕለትም ከጥናት አቅራቢዎች መካከል ፕሮፌሰር ዴቪድ ፊልፕሰን ‹‹በማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል ይህን ዐውደ ጥናት በማዘጋጀቱ በቤተ ክርስቲያኒቱ ዙሪያ የሚሠሩ ምርምሮችን ከሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን ልጆች ጋር ለመወያየት እድል ፈጥሮልኛል›› በማለት አስተያየት ከሰጡ በኋላ ዐውደ ጥናቱን ያዘጋጀውን ማኅበረ ቅዱሳንን አመስግነዋል፡፡ ሌሎች ጥናት አቅራቢዎችና ተሳታፊዎችም በጉባኤው እንደ ተደሰቱ ገልጸው ወደፊትም ይኽን ዓይነቱ የጥናት ጉባኤ ተጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበዋል፡፡

በመጨረሻም ለዚህ ዓለም አቀፍ ጉባኤ መሳካት አስተዋጽዖ ላደረጉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ ለሉንድ ደብረ መዊዕ ቅዱስ ሚካኤል ሰበካ ጉባኤ፣ ለሉንድ ዩኒቨርሲቲ፣ ለፕሮፌሰር ሳሙኤል ሩቢንሰን፣ ጥናታዊ ጽሑፍ ላቀረቡና መልእክት ላስተላለፉ ምሁራን፣ ለተጋባዥ እንግዶች እና በጉባኤው ለተሳተፉ ምእመናን የዐውደ ጥናት ዝግጅት ኮሚቴው ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር አምሳሉ ተፈራ በኮሚቴው፤ ዲያቆን ዓለምነው ሽፈራው ደግሞ በአውሮፓ ማእከል ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

ቅዱስ ሩፋኤል

ቅዱስ ሩፋኤል ሊቀ መላእክት

በዲያቆን ዮሴፍ ይኵኖአምላክ

ጳጕሜን ፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ወርኀ ጳጕሜን የዓለም ፍጻሜ መታሰቢያ ተደርጋ ትታሰባለች፡፡ በዚህ የተነሣ ምእመናን በጾምና በጸሎት (በሱባዔ) ያሳልፏታል፡፡ በተለይም በቅዱስ ሩፋኤል ዕለት ሰማያት የሚከፈቱበት (ርኅዎተ ሰማይ) መኾኑን በማመን ምእመናን ጸሎታቸውን ከምንጊዜውም በበለጠ ያቀርባሉ፡፡ ወደ ወንዞች በመሔድና በሚዘንበው ዝናብ ይጠመቃሉ፡፡ ወርኀ ጳጕሜን የጌታችን ምጽአት የሚታሰብባት በመኾኗ የሚዘመረው መዝሙር፣ የሚነበቡ ምንባባትና ቅዱስ ወንጌሉ እንደዚሁም የሚሰበከው ምስባክ ይህንኑ ምሥጢር የሚያሳዩ ናቸው፡፡

በወርኀ ጳጉሜን ከሚታሰቡ እና ከሚከበሩ በዓላት መካከል በየዓመቱ ጳጕሜን ፫ ቀን የሊቀ መላእክት የቅዱስ ሩፋኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል በመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት በልዩ ልዩ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ይከበራል፡፡ የቅዱስ ሩፋኤል በዓሉ የሚከበርባቸው ምክንያቶችም ሁለት ናቸው፤ እነርሱም አንደኛው በዓለ ሢመቱን ምክንያት በማድረግ ሲኾን፣ ሁለተኛው ደግሞ ቅዳሴ ቤቱ ነው፡፡ ‹ሩፋኤል› የሚለው የስሙ ትርጓሜ ‹ደስ የሚያሰኝ፣ ቸር፣ መሐሪ፣ ቅን የዋህ› ማለት ነው፡፡ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል ያለ ማቋረጥ ፈጣሪያቸው ልዑል እግዚአብሔርን ከሚያመሰግኑ ቅዱሳን መላእክት አንዱ ነው፡፡ ‹‹ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ›› እንዲል (ጦቢት ፲፪፥፲፭)፡፡

የሰው ልጆች ከተያዙበት የኀጢአት ቍስል ይፈወሱ ዘንድ በአማላጅነቱና በጸሎቱ የማይለይ መልአክ ነው፡፡ ‹‹በበሽታ ላይ በሰው ልጆችም ቍስል ላይ የተሾመው ቅዱስ ሩፋኤል ነው›› በማለት ሄኖክ ከእግዚአብሔር መልአክ ያገኘውን የምስክርነት ቃል ጽፏል (ሄኖክ ፲፥፲፫)፡፡ ቅዱስ ሩፋኤል በሰውነታችን ላይ የሚወጣውን ደዌም ኾነ ቍስል ይፈውስ ዘንድ ከልዑል እግዚአብሔር ሥልጣን ተሰጥቶታል፡፡ ‹‹በሰው ቍስል ላይ የተሾመ ከከበሩ መላእክት አንዱ ቅዱስ ሩፋኤል ነው›› እንዳለ ሄኖክ (ሄኖክ ፮፥፫)፡፡ ለቈሰሉ ፈውስን የሚያሰጣቸው፤ ላረገዙ ሴቶች ረዳታቸው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ ሴት በፀነሰችበት ወቅት ቅዱስ ሩፋኤል አይለያትም፡፡ ሕፃኑ (ኗ በማኅፀን እያለ (ች) ተሥዕሎተ መልክዕ (በሥላሴ አርአያ መልኩ /ኳ/ መሳል) ከጀመረበት ቀን አንሥቶ እስከሚወለድበት ቀን ድረስ ቅዱስ ሩፋኤል በጥበቃው አይለያቸውም፡፡ በመውለጃቸው ቀን ሴቶች ከሚደርስባቸው ጭንቀትና ሕመም ስሙን ጠርተው ይማጸኑታል፡፡ ፈታሔ ማኅፀን ነውና ቅዱስ ሩፋኤልም ጭንቀታቸውን ያቀልላቸዋል፡፡

አስማንድዮስ የተባለ ጋኔን በወለተ ራጉኤል ላይ አድሮ ባሎቿን እየገደለ ቢያሰቃያት ቅዱስ ሩፋኤል ጋኔኑን አስጨንቆ አስወጥቶላታል (ጦቢት ፫፥፰-፲፯)፡፡ ቅዱስ ሩፋኤል ‹‹ዳግመኛም እግዚአብሔር ሩፋኤልን፣ አዛዝኤልን እጁን እግሩን አስረህ በጨለማ ውስጥ ጣለው አለው›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሄኖክ ፫፥፭-፯)፡፡ ለቃየን ልጆች ሰይፍና ሾተል መሥራትን፣ የምንዝር ጌጥ ማጌጥን፣ መቀንደብን ያስተማረ አዛዝኤል የተባለውን ጋኔን በእሳት ሰይፍ እየቀጣ በረቂቅ አስሮ ወደ ጥልቁ የጣለው ይኸው መልአክ ቅዱስ ሩፋኤል ነው (ሄኖክ ፪፥፲፰)፡፡ የጦቢትን ልጁ ጦቢያን በሰው አምሳል ተገልጦ ከተራዳው በኋላ ወደ ሰማይ በሚያርግበት ጊዜ ራሱን ሲገልጥ ‹‹የቅዱሳንን ጸሎት ከሚያሳርጉ ወደ ከበረ ወደ ገነነ ወደ እግዚአብሔር ጌትነትም ከሚያገቡ ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ አላቸው›› (ጦቢት ፲፪፥፲፭)፡፡

በቅዱስ ሩፋኤል ተራዳዒነት ከተደረጉ ተአምራት መካከል በእስክንድርያ አቅራቢያ በምትገኝ ደሴት በታነጸች ቤተ ክርስቲያኑ ያደረገው ተአምር አንደኛው ነው፡፡ በመጽሐፈ ስንክሳር እና በድርሳነ ሩፋኤል እንደ ተጻፈው ብዙ ምእመናን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እያሉ ቤተ ክርስቲያኒቱ ፈጽማ ተናወጠች፤ ያቺ ደሴት በታላቅ አንበሪ ጀርባ ላይ የቆመች ናትና፡፡ የሰዎች ብዛትም በከበደው ጊዜ ዓሣ አንበሪው ቤተ ክርስቲያኒቱን ያፈርሳት ዘንድ ሰይጣን አነሣሣው፡፡ ምእመናኑም ወደ ክብር ባለቤት እግዚአብሔር በከበረ መልአክ ሩፋኤል ስም ጮኹ፡፡ ያን ጊዜ ቅዱስ ሩፋኤል ያንን አንበሪ በጦሩ ወግቶ ‹‹እግዚአብሔር አዝዞሃልና ከቦታህ ሳትናወጥ ጸጥ ብለህ ቁም!›› ባለው ጊዜ አንበሪው ጸጥ ብሎ ቆሟል፡፡ በውስጧም ድንቆች ተአምራቶች ተገልጠዋል፡፡ ለሕሙማንም ፈውስ ኾኗል፡፡ የቅዱስ ሩፋኤል ተራዳዒነት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የ፳፻፲ ዓ.ም ዘመን መለወጫን አስመልክቶ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ የሰጡት ቃለ በረከት

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የ፳፻፲ ዓ.ም ዘመን መለወጫን አስመልክቶ የሰጡትን ሙሉዉን ቃለ በረከት እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ

ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ዘተናገረ በበዓለ ርእሰ ዐውደ ዓመት ዘዕሥራ ምእት ወዐሠርቱ ዓመተ ምሕረት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

  • በአገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፤
  • ከአገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ
  • የአገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤
  • በሕመም ምክንያት በየጠበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤
  • እንደዚሁም የሕግ ታራሚዎች ኾናችሁ በየማረሚያ ቤተ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፤

የዘመናትና የፍጥረታት ፈጣሪ የኾነው እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ከዘመነ ማቴዎስ ሁለት ሺሕ ዘጠኝ ዓመተ ምሕረት ወደ ዘመነ ማርቆስ ሁለት ሺሕ ዐሥር ዓመተ ምሕረት በሰላም አደረሳችሁ፡፡

“አንሶስዉ እንዘ ብክሙ ብርሃን፤ ብርሃን ሳለላችሁ በብርሃን ተመላለሱ” (ዮሐ. ፲፪፥፴፭)

የብርሃን ጸጋ ለሰው ልጆች ወይም በአጠቃላይ ለፍጥረታት ዅሉ ከተሰጠው የእግዚአብሔር ስጦታዎች ትልቁ ነው፤ ብርሃን የሥራ መሣሪያ ነው፤ ብርሃን የመልካም ነገር ሁሉ ተምሳሌት ነው፡፡ እግዚአብሔር ራሱ በባሕርዩ ብርሃን ከመኾኑም ሌላ በእርሱ ዘንድ የማይጠፋ ብርሃን እንዳለ በቅዱስ መጽሐፍ ተገልጿል፡፡ የሰው ልጅ ከወዲያ ወዲህ፣ ከወዲህ ወዲያ ተንቀሳቅሶ፣ ነግዶ፣ አርሶ፣ ሠርቶ፣ ተምሮና አስተምሮ ለኑሮው የሚያስፈልገውን ዅሉ ለማግኘት ብርሃን የግድ ያስፈልጋል፡፡

ከዚኽም ጋር ሙሉ ጤና፣ ቀና የኾነ አእምሮ፣ ሰላምና ፍቅር ለሰው ልጅ ብልጽግና ወሳኝ ቦታ አላቸው፡፡ እነዚህ በሰው ልጅ መንፈሳዊና ሥጋዊ ሕይወት ላይ ያላቸው ጸጋ እጅግ የላቀ በመኾኑ በቅዱስ መጽሐፍ አገላለጽ ብርሃን እየተባሉ ይጠቀሳሉ፡፡ እንደዚሁም ዕድሜና መልካም ዘመን በተመሳሳይ አገላለጽ ብርሃን ተብሎ ይመሠጠራል፡፡ ምክንያቱም ብርሃን በሌለበት ኹኔታ ምንም ሥራ መሥራት እንደማይቻል ሰላማዊ ዘመን ከሌለም ልማትና ዕድገት ማስመዝገብ አይቻልማና ነው፡፡ በመኾኑም ዕድሜና ዘመንም ሌላው ታላቁ የእግዚአብሔር ብርሃን ነው፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ብርሃን ሳለላችሁ በብርሃን ተመላለሱ” ሲል የዕድሜና የጊዜ ብርሃንነትን ማመልከቱ እንደ ኾነ ዐውደ ምንባቡ በግልጽ ያሳያል፡፡ ምክንያቱም እርሱ በዚኽ ዓለም በመምህርነት የተገለጸበት ዘመን ወደ መጠናቀቁ እየተቃረበ በነበረበት ጊዜ የተናገረው ከመኾኑ ጋር ባለችው አጭር ጊዜ የትምህርት ዕድሜ ወይም ዘመን ሰዎች በእርሱ ብርሃንነት እንዲያም የቀሰቀሰበትና ያስተማረበት ትምህርት ነው፡፡ በእርግጥም ላስተዋለውና በሥራ ለተጠቀመበት ጊዜ ታላቁ ብርሃን ነው፡፡ ጊዜ ሲቀና ነገሩ ዅሉ ብርሃን ይኾናል፡፡ ጊዜው ከጨለመ ደግሞ ዙሪያው ዅሉ ጨለማ ይኾናል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት

ዕድሜያችን ወይም ዘመናችን በሕይወታችን ውስጥ ለልማትም ኾነ ለጥፋት፣ ለጽድቅም ኾነ ለኀጢአት፣ ለትንሣኤም ኾነ ለውድቀት መሣሪያነቱ የታወቀ ነው፡፡ ምክንያቱም ዅሉም የሚሠራውና የሚከናወነው በጊዜው ነውና፡፡ በዘመናት ውስጥ ብርሃናውያን የኾኑ ዓመታት እንደ ነበሩ ዅሉ ጽልመታውያን የኾኑ ዓመታትም በአገራችንም ኾነ በሌላው ዓለም እንደ ነበሩ እናውቃለን፡፡ እነዚኽ ተቃራኒ የኾኑ ነገሮች በየፊናቸው ለሰው ልጆች ያተረፉት ስጦታም በስማቸው ልክ እንደ ኾነ ይታወቃል፡፡ ይኹን እንጂ ዘመናትን ብርሃውያን ወይም ጽልመታውያን እንዲኾኑ በማድረግ ረገድ የሰው ልጅ ሚና ትልቅ እንደኾነ የማይካድ ነው፡፡

የሰው ልጅ የማስተዋልና የመቻቻል፣ የመታገሥና የመወያየት፣ የፍቅርና የስምምነት፣ የሰላምና አንድነት ጠቃሚነትን ዘንግቶ በስሜትና በወቅታዊ ትኩሳት፣ እንደዚሁም እግዚአብሔርን የሰላም ድምፅ አልሰማ ብሎ በራስ ወዳድነትና በስግብግብነት ተሸንፎ ወደ ትርምስ ሲገባ ዘመኑ ጽልመታዊ መኾኑ አይቀሬ ነው፡፡ በሰው ችኩልና ደካማ አስተሳሰብ የተጨናነቀ ጽልመታዊ ዘመን ከውድመትና ከጥፋት በቀር አንዳችም ትርፍ እንደሌለው ከአገራችን ተሞክሮ የበለጠ መምህር አይኖርም፡፡

በሌላ በኩል ሰዎች ከእርስ በርስ ግጭት ተላቀው ሰላምንና ፍቅርን፣ አንድትንና እኩልነትን፣ መቻቻልንና መስማማትን፣ መወያየትንና መቀራረብን፣ ወንድማማችነትንና መከባበርን ያረጋገጠ፣ ትዕግሥትና አስተዋይነት የማይለየው የእግዚአብሔርን ድምፅ በመከተልና አእምሮን በማስፋት መኖር ሲጀምሩ ዘመኑ ብርሃናዊ እንደሚኾን፣ ልማቱና ዕድገቱም እንደሚፈጥንና እንደሚረጋገጥ አሁንም በአገራችን ወቅታዊ ተሞክሮ ተረድተዋል፡፡ ይኽ ዅሉ እውነታ የሚያሳየው የዘመን ብርሃንነትና ጽልመትነት የሚወሰነው እኛ ሰዎች በምናውጠነጥነው አስተሳሰብና በምናደርገው እንቅስቃሴ እንደ ኾነ ማስተዋል ተገቢ ነው፡፡ ለዚኽም ነው ሓላፊነቱም ተመልሶ ወደ እኛ የሚመጣው፡፡

ጌታችንም ምርጫውንና ውሳኔውን ለእኛ ትቶ “ብርሃን ስላላችሁ በብርሃን ተመላለሱ” በማለት ገለጻውንና ትምህርቱን ብቻ መናገሩ ከዚህ የተነሣ እንደ ኾነ ማስተዋል ይገባል፡፡ ከእነዚህ ከሁለቱ የሚሻለንን መምረጥና መከተል የእኛ ፈንታ ነው፡፡ ምርጫችን ሰላምና አንድነት ከኾነ ዘመኑ ብርሃን ነው፤ ተቃራኒው ከኾነ ደግሞ የኋልዮሽ ጉዞ ይኾናል፡፡ ስለ ኾነም ምርጫችን ሰላምና አንድነት እንዲኾን ዅላችንም ተስማምተን መወሰን አለብን፡፡

ማንም ሰው ብርሃንና ጨለማ ጎን ለጎን ቀርበውለት የትኛውን ትመርጣለህ የሚል ጥያቄ ቢቀርብለት ያለማመንታት ብርሃኑን እንደሚመርጥ ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ ችግሩ ሰዎች ይህን ግልጽና ጠቃሚ ምርጫ ተቀብለው ተጠቃሚ እንዳይኾኑ ብዙ የሚያታልሉና በድብብቆሽ የሚመላለሱ አካላት በመካከሉ ይገቡና ጨለማውን ብርሃን፣ ብርሃኑንም ጨለማ አስመስለው ሰውን ወደ ገደል መክተታቸው ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ብርሃናዊና መልካም የኾነ ምርጫችንን ጥያቄ ውስጥ እንዲገባ ያድርጉታል፡፡ እኛ ሰዎች አእምሯችንን በሚገባ መጠቀም ያለብን እዚኽ ላይ ነው፡፡ ማለትም እኛው ራሳችን የሚጠቅመንና የማይጠቅመንን የመለየት ዓቅም ስላለን ዓቅማችንን ተጠቅመን ለዘላቂ ጥቅማችንና ለትክክለኛ ምርጫችን መወገን ይኖርብናል ማለት ነው፡፡

ሰዎች የኾን ዅላችን ባለ አእምሮዎች ኾነን ተፈጥረናል፡፡ አእምሮ ከእግዚአብሔር ጋር የሚያመሳስለን ስለ ኾነ ከሀብት ዅሉ የበለጠ ሀብት ነው፡፡ ይህንን አእምሯችንን ካዳመጥነውና ከተከተልነው ሐቁን አይስትም፡፡ አመዛዝኖ፣ ገምግሞ፣ ለክቶ ጠቃሚውን ነገር ከልባችን ውስጥ ቁጭ ያደርግልናል፡፡ ነገር ግን ትዕግሥትን፣ ማገናዘብን፣ ቆም ብሎ ማሰላለሰልን፣ ምክንያታዊ መኾንን፣ ማመዛዘንን፣ ፈሪሀ እግዚአብሔርን፣ ፈቃደ እግዚአብሔርን መከተልን ይፈልጋልና እነዚኽን እንደ ግብአት አድርገን ልናቀርብለት ይገባል፡፡ ይህንን መጠቀም ስንችል የዘመናችንና የዕሜያችን ብርሃን ዋስትና ይኖረዋል፡፡ ጨለማም አያሸንፈውም፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት

ለዐሥር ዓመታት ያህል የተጓዝንበት የሦስተኛው ሺሕ ወይም ሚሊኒየም ዓቢይ ዘመን ለኢትዮጵያ አገራችን ብርሃናዊ ዘመን የፈነጠቀበት ወቅት ነው፡፡ ምክንያቱም በዚህ ዘመን ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ያልተነካ ሀብታችን እርሱም የዓባይ ወንዝ ሀብታችንን ለመቋደስ የሚያስችል ግዙፍ የልማት ሥራ ተጀምሮ ወደ መጠናቀቅ እየተቃረበ ያለበት እጅግ ብርሃናዊ ዘመን በመኾኑ ነው፡፡

በሠለጠነው የምዕራቡ ዓለም ካልኾነ በቀር በአፍሪካ ምድር ለዚያውም በድርቅ፣ በረኃብና በጦርነት ትታወቅ በነበረችው ኢትዮጵያ ይኾናሉ ተብለው የማይታሰቡ እጅግ ግዙፍ የኾኑና የሕዝባችንን መሠረታዊ የዕድገት ለውጥ የሚያረጋግጡ የኮንስትራክሽንና የኢንዱስትሪ፣ የትምህርትና የጤና ተቅዋማት በፍጥነት እየገሠገሡ መገኘት በዚህ ብርሃናዊ ዘመን የዕለት ተዕት ትእይንት እንደ ኾኑ በዓይን እየታየ ነው፡፡ ይኽ ጸጋ እንዲሁ ያለ መሥዋዕትነት የተገኘ ሳይኾን እኛ ኢትዮጵያውያን ከዅሉ በላይ ሰላምንና ልማትን መርጠን በአንድነት ወደ ብርሃናዊ አስተሳሰብ ስለ ገባን ነው፡፡ እግዚአብሔርም “በብርሃን ተመላሱ” ያለው ይኽን ለማመልከት ነውና በዚህ ምክንያት ትክክለኛ ምርጫችንን እርሱ ስለባረከልን የልማትና የዕድገት ተምሳሌት መኾን እንደቻልን አንስተውም፡፡

ዛሬም ወደማንወደውና ወደማንመርጠው ጨለማ ሊከቱን የሚሹ እንደ ኤች አይ ቪ ኤድስና ሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውር፣ እንደዚሁም በሕዝባችን መካከል መለያየትና መቃቃር ሊያስከትሉ የሚችሉ አፍራሽ ድርጊቶች ብቅ ብቅ በማለት እየተፈታተኑን እንደ ኾኑ መዘንጋት የለበትም፡፡ እነዚኽ ዅሉ በተግባር ያየናቸው የሕዝባችን ቀንደኛ ፀርና የጨለማ አበጋዞች፣ የልማታችንና የሰላማችን ዕንቅፋቶች ናቸውና ሕዝቡ በተለመደው ሃይማኖታዊና አርቆ ማሰብ ኀይሉ እንዲመክታቸው በዚህ አጋጣሚ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡

በመጨረሻም

የዛሬ ዐሥር ዓመት “ታላቅ ነበርን ታላቅም እንኾናለን” በማለት ለሦስተኛው ሺሕ ወይም ሚሊኒየም ዓቢይ ክፍለ ዘመን የገባነውን ቃል በማደስ በአዲሱ ዓመት ካለፈው ዓመት በበለጠ ጠንክረን በመሥራት፣ ልማታችንንና ዕድገታችንን በፍጥነት በማሳደግ፣ የኤች አይ ቪ ኤድስ በሽታን ባለን የተሞክሮ አሠራር በመመከት፣ እንደዚሁም ሕገ ወጥ ዝውውርን፣ አገርንና ሕዝብን የሚጎዳ ድርጊትን በማክሸፍ፣ በሃይማኖትና በሰላም መርሕ በመመራት አዲሱን ዘመን ብርሃናዊ እንድናደርገው መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

አዲሱን ዘመን የሰላም፣ የፍቅርና የብልጽግና ያድርግልን፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን ኢትዮጵያንና ሕዝባችንን ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

መስከረም ፩ ቀን ፳፻ወ፲ ዓ.ም

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

ዘመነ ክረምት – ክፍል ሰባት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ጳጕሜን ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የማኅበረ ቅዱሳን ድረ ገጽ ተከታታዮች! በክፍል ስድስት ዝግጅታችን አራተኛውን የዘመነ ክረምት ንዑስ ክፍል ማለትም ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን እና መዓልትን መነሻ አድርገን ወቅቱን ከሕይወታችን ጋር በማዛመድ መንፈሳዊ ትምህርት አቅርበን ነበር፡፡ በዚህ ዝግጅት ደግሞ አምስተኛውን የዘመነ ክረምት ንዑስ ክፍል (ቀዱስ ዮሐንስን) የሚመለከት አጭር ትምህርት ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡ መልካም ንባብ ይኹንላችሁ!

፭. ዮሐንስ

ከመስከረም ፩ – ፰ ቀን (ከዮሐንስ እስከ ዘካርያስ) ያለው አምስተኛው ክፍለ ክረምት ‹ዮሐንስ› በመባል ይታወቃል፡፡ ይህ ክፍለ ጊዜ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለማጥመቅ የተመረጠው፣ የዓዋጅ ነጋሪው መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ትምህርቱ፣ ጥምቀቱ፣ ምስክርነቱ፣ አገልግሎቱ፣ ክብሩ፣ ቅድስናው፣ ገድልና ዕረፍቱ በአጠቃላይ ዜና ሕይወቱ ከአዲሱ ዓመት ጋር እየተጣጣመ የሚዳሰስበት የብሥራት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ሳምንት የቅዱስ ዮሐንስን አገልግሎት የሚመለከቱ ትምህርቶች በቤተ ክርስቲያን በስፋት ይቀርባሉ፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ አዲስ ዓመት በመጣ ቍጥር የቅዱስ ዮሐንስ ክብረ በዓልም አብሮ ይዘከራል፡፡

ሕዝበ ክርስቲያኑም ለአዲሱ ዓመት ብቻ ሳይኾን ‹‹ለቅዱስ ዮሐንስ በዓል እንኳን በሰላም አደረሳችሁ›› እያሉ መልካም ምኞታቸውን ለወዳጅ ዘመዶቻቸው መግለጻቸው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት የቅዱስ ዮሐንስ በዓል ከአዲስ ዓመት መባቻ ጋር በአንድነት ሲከበር ለመቆየቱ ማስረጃ ነው፡፡ ይኸውም የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ከጳጕሜን ፩ ቀን ጀምሮ በእስር ቤት ከቆየ በኋላ መስከረም ፪ ቀን በሰማዕትነት ዐርፏል፡፡ ቅዱሱ የሐዲስ ኪዳን አብሣሪ ነውና፣ ደግሞም ዕለቱ ቃል ኪዳን የተቀበለበት ቀን ነውና ስሙና ግብሩ ከዘመን መለወጫ ጋር አብሮ ይታወስ ዘንድ በዓሉ መስከረም ፩ ቀን በሥርዓተ ማኅሌት ይከበራል፡፡ ለዚህም ነው – ሊቃውንቱ ‹‹ርእሰ ዐውደ ዓመት ዮሐንስ ወላዴ መጥቅዕ ወአበቅቴ›› እያሉ የአዲስ ዓመት መጀመርያ፣ የመጥቅዕ እና አበቅቴ መነሻ መኾኑን በሚገልጽ ኃይለ ቃል ቅዱስ ዮሐንስን የሚያወድሱት፡፡

ታሪኩን ለማስታወስ ያህል ዮሐንስ ማለት ‹እግዚአብሔር ጸጋ ነው› ማለት ነው፡፡ ትርጓሜ ወንጌልም ፍሥሐ ወሐሴት (ተድላና ደስታ) ይለዋል፤ ወላጆቹ በእርሱ መወለድ ተደስተዋልና (ሉቃ. ፩፥፲፬)፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ የካህኑ ዘካርያስና የቅድስት ኤልሳቤጥ ልጅ ነው፡፡ ቅድስት ኤልሳቤጥ መካን (ካ ይጠብቃል) በመኾኗ እነዚህ የእግዚአብሔር ሰዎች ልጅ አልነበራቸውም፡፡ ልጅ ይሰጣቸው ዘንድም እግዚአብሔርን ዘወትር በጸሎት ይማጸኑት ነበር (ሉቃ. ፩፥፭-፯)፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን የካህኑ ዘካርያስ ጸሎቱ እንደ ተሰማና ሚስቱ ቅድስት ኤልሳቤጥ እንደምትወልድ፤ ስሙን ዮሐንስ እንደሚለው፤ በመወለዱ ብዙዎች እንደሚደሰቱ፤ ልጁም በእግዚአብሔር ፊት ታላቅ እንደሚኾን፤ የወይን ጠጅና የሚያሰክር መጠጥ እንደማይጠጣ፤ እንደዚሁም ከእናቱ ማኅፀን ጀምሮ መንፈስ ቅዱስ እንደሚሞላበት የእግዚአብሔር መልአክ ለዘካርያስ ነገረው (ሉቃ.፩፥፰-፲፯)፡፡ በዚህ ቃለ ብሥራት መሠረት ቅዱስ ዮሐንስ ሰኔ ፴ ቀን ተወለደ፡፡ ሕፃኑ ዮሐንስም አደገ፤ በመንፈስም ጠነከረ፤ ለእስራኤል እስከታየበት ቀን ድረስ በምድረ በዳ ኖረ (ሉቃ. ፩፥፹)፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ፴ ዓመት ሲሞላውም በነቢዩ በኢሳይያስ ቃል ‹‹መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ!›› እያለ እየሰበከ በዮርዳኖስ ዙሪያ ወዳለው አገር ዅሉ ወጣ (ሉቃ. ፫፥፫-፮)። የይሁዳ አገር ሰዎች ዅሉ ኀጢአታቸውን እየተናዘዙ ከእርሱ ይጠመቁ ነበር። እርሱም ቃለ ወንጌልን ይሰብክላቸው ነበር (ሉቃ. ፫፥፯-፲፬)፡፡ በመጨረሻም ‹‹ድንበር አታፍርሱ፤ ዋርሳ አትውረሱ›› እያለ ንጉሡ ሄሮድስንና ሄሮድያዳን በመገሠፁ ምክንያት አንገቱን በሰይፍ ተቈርጦ በሰማዕትነት ዐርፏል፡፡ ካረፈ በኋላም የራስ ቅሉ ክንፍ አውጥቶ በዓለም እየተዘዋወረ ፲፭ አምስት ዓመት ወንጌልን አስተምሯል፡፡

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ምን ልታዩ ወደ ምድረ በዳ ወጣችሁ? … ነቢይን? አዎን ይህ ከነቢይም ይበልጣል።እነሆ መንገድህን በፊትህ የሚጠርግ መልክተኛዬን በፊትህ እልካለሁተብሎ የተጻፈለት እርሱ ነው፤ ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሣም፤ ልትቀበሉትስ ብትወዱ ይመጣ ዘንድ ያለው ኤልያስ ይህ ነው፤ የሚሰማ ጆሮ ያለው ይስማ›› በማለት የቅዱስ ዮሐንስን ታላቅነት ለሕዝቡ ተናግሯል (ማቴ. ፲፩፥፱-፲፩)። እንደዚሁም ቅዱስ ዮሐንስን ከነቢዩ ኤልያስ ጋር በማመሳሰል ስለ አገልግሎቱ አስተምሯል (ማቴ. ፲፩፥፪-፲፱)።

ሊቁም ከመላእክት፣ ከነቢያት፣ ከካህናት፣ ከሐዋርያት መካከል እንደርሱ መለኮትን ለማጥመቅ የተመረጠ አለመኖሩን በመጥቀስ ‹‹ዮሐንስ ከማከ ሶበ ፈተዉ ወጽሕቁ፤ እሳተ ነዳዴ ኢተክህሎሙ ያጥምቁ፤ ራጉኤል በትጋሁ ወኢዮብ በጽድቁ፤ ዮሐንስ ሆይ! ራጉኤል በትጋቱ፣ ኢዮብም በጽድቁ ቢመኙም ኾነ ቢጨነቁ እንደ አንተ የሚነድ እሳትን (መለኮትን) ሊያጠምቁ አልተቻላቸውም›› ብሎ ታላቅነቱን መስክሮለታል (መልክአ ዮሐንስ መጥምቅ፣ ለአዕይንቲከ)፡፡

በአጠቃላይ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ከአዲስ ኪዳን አበው አንዱ የኾነ፣ ንጹሓን ነቢያት፣ ቅዱስ ገብርኤልና አባቱ ዘካርያስ ትንቢት የተናገሩለት፣ ከሕፃንነቱ ጀምሮ ቅኑት እንደ ገበሬ፣ ጽሙድ እንደ በሬ ኾኖ እግዚአብሔርን ያገለገለ፣ በፍጹም ልቡ ዓለምን የናቀ፣ ከተድላዋና ከደስታዋም የተለየ፣ አምላክን ለማጥመቅ የታደለ ሐዋርያ፣ መምህር፣ ሰማዕት፣ ባሕታዊ፣ ነቢይ፣ ጻድቅ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ሰኔ ፴ ቀን የተወለደበት፤ መስከረም ፩ ቀን ቃል ኪዳን የተቀበለበት፤ መስከረም ፪ ቀን በሰማዕትነት ያረፈበት፤ ጥር ፲፩ ቀን ጌታችንን ያጠመቀበት፤ የካቲት ፴ ቀን ራሱ የተገኘችበት፤ ሚያዝያ ፲፭ ቀን ራሱ ያረፈችበት (ነፍሱ የወጣችበት)፤ ሰኔ ፪ ቀን ደግሞ ፍልሰተ ዐፅሙ (ዐፅሙ የፈለሰበት) በዓል በቤተ ክርስቲያናችን ይከበራል፡፡ የቅዱስ ዮሐንስ ሕይወቱና ትምህርቱ፣ ያደረጋቸው ድንቆችና ተአምራት፣ እንደዚሁም እግዚአብሔር የሰጠው ቃል ኪዳንና አገልግሎቱን በሰማዕትነት መፈጸሙ በመጽሐፈ ስንክሳር፣ በትርጓሜ ወንጌል (ወንጌለ ሉቃስ) እና በገድለ ዮሐንስ መጥምቅ በሰፊው ተጽፏል፡፡

እንግዲህ እኛም እንደ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ከኀጢአት ተለይተን፣ ራሳችንን ለጽድቅ ሥራ አስገዝን፣ በንጽሕና ኾነን አዲሱን ዓመት ለመቀበል ከዅሉም በላይ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ እንዘጋጅ፡፡

ይቆየን

ወርኀ ጳጕሜን

በዲያቆን ዳንኤል ክብረት

ጳጕሜን  ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የኢትዮጵያን የዘመን አቈጣጠር ለየት ከሚያደርጉት ነጥቦች አንዱ ‹ጳጕሜን› የምትባል ዐሥራ ሦስተኛ ወር መኖሯ ነው፡፡ ‹ጳጕሜ› ማለት በግሪክ ቋንቋ ‹ጭማሪ› ማለት ሲኾን፣ ወርኀ ጳጕሜን ዓመቱ በሠላሳ ቀናት ሲከፈል የሚተርፉት ዕለታት ተሰባስበው የሚያስገኟት፤ ወይም በየዕለቱ በፀሐይና በጨረቃ አቈጣጠር መካከል የሚፈጠሩት ልዩነቶች ተሰባስበው የተከማቹባት ተጨማሪ ወር ናት፡፡ ወርኀ ጳጕሜን የቤት ኪራይና የወር ደመወዝ የማንከፍልባትና የማንቀበልባት፤ መብራትና ውኃ ግን ከነሐሴ ወር ጋር ጨምረው የሚያስከፍሉባት፤ ሲሻት አምስት፣ ሲያስፈልጋት ስድስት፣ አልፎ አልፎ ሰባት የምትኾን ወር ናት፡፡ ከዐሥራ ሁለቱ የኢትዮጵያ ወሮች መካከል ወርኀ ጳጕሜን በብዙ መንገድ የተለየች ናት፡፡ በአንድ በኩል በጣም ትንሿ ወር ናት፡፡ ሲቀጥልም ወርኃዊ በዓላት የማይውሉባት ወር ናት፡፡ ደግሞም ከሌሎች ወሮች በተለየ መልኩ የቀኖቿ መጠን የሚቀያየሩ ብቸኛ ወር ናት፡፡ ከሌሎች የኢትዮጵያ ወሮች በተለየም ስሟ ኢትዮጵያዊ ያልኾነ ወር ናት፡፡ በሁለት ዘመናት መካከል እንደ መሸጋገሪያ የምትታይም ናት፡፡

ዓመቱ በዐውደ ፀሐይ ሲለካ 365 ቀናት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት ሲኾን፣ በጨረቃ ሲለካ ደግሞ 354 ቀናት ከ22 ኬክሮስ፣ ከ1 ካልዒት፣ ከ36 ሣልሲት፣ ከ52 ራብዒት፣ ከ48 ኀምሲት ነው፡፡ በሁለቱ አቈጣጠር መካከል (በፀሐይና በጨረቃ) በዓመት ውስጥ ያለው ልዩነት 11 ቀናት ከ7 ኬክሮስ ይኾናል፡፡ በዘመን አቈጣጠራችን ከዕለት በታች የምንቈጥርባቸው ስድስት መለኪያዎች አሉን፡፡ እነዚህም ኬክሮስ፣ ካልዒት፣ ሣልሲት፣ ራብዒት፣ ኀምሲትና ሳድሲት ናቸው፡፡ 60 ሳድሲት 1 ኀምሲት፣ 60 ኀምሲት 1 ራብዒት፣ 60 ራብዒት 1 ሣልሲት፣ 60 ሣልሲት 1 ካልዒት፣ 60 ካልዒት 1 ኬክሮስ ነው፡፡ 60 ኬክሮስ 1 ዕለት፤ 1 ኬክሮስ ደግሞ 24 ደቂቃ ነው፡፡ ወርኀ ጳጕሜንን ለማግኘት የሚረዳንም የየዕለቱን ልዩነታቸውን መመልከቱ ነው፡፡ በየዕለቱ በጨረቃና በፀሐይ መካከል ያለው የጊዜ ስሌት 1 ኬክሮስ ከ52 ካልዒት ከ31 ሣልሲት ይኾናል፡፡ ይህም ማለት 5 ሰዓት ከ48 ደቂቃ ከ46 ካልዒት ነው፤ ይህ ልዩነት በአንድ ወር ምን ያህል እንደሚደርስ ለማወቅ በ30 ብናበዛው 30 ኬክሮስ ከ1560 ካልዒት፣ ከ930 ሣልሲት ይኾናል፡፡ የዓመቱን ለማግኘት ደግሞ በ12 ብናበዛው 360 ኬክሮስ ከ18720 ካልዒት፣ ከ11160 ሣልሲት ይመጣል፡፡

360 ኬክሮስ ለ60 ሲካፈል 6 ዕለታትን ይሰጠናል፡፡ 18720 ካልዒትን በስድሳ በማካፈል 312 ኬክሮስን እናገኛለን፡፡ ይኸውም ትርፉን 12 ኬክሮስ ትተን 300ውን ኬክሮስ ለ60 በማካፈል 5 ዕለት እናገኛለን ማለት  ነው፡፡ ውጤቱም 5 ዕለት ከ12 ኬክሮስ ይኾናል፡፡ 11160 ሣልሲትን ለ60 ብናካፍለው 186 ካልዒት ወይም ደግሞ 3 ኬክሮስና 6 ካልዒት ይኾናል፡፡ ከላይ ኬክሮስን በዓመቱ ቀናት አባዝተን ያገኘነው 6 ዕለት ‹ሕጸጽ› ይባላል፡፡ ፀሐይና ጨረቃን እኩል መስከረም አንድ ላይ ዓመቱን ብናስጀምራቸው ፀሐይ የወሯ መጠን ምንጊዜም 30 ሲኾን፣ ጨረቃ ግን በአንደኛው ወር 29፤ በሌላኛው ወር ደግሞ 30 ስለምትኾን ዓመቱ እኩል አያልቅም፡፡ የጨረቃ ዓመት የሚያልቀው ነሐሴ 24 ቀን ነውና፡፡ ይህም ማለት ጨረቃ በሁለት ወር አንድ ጕድለት ታመጣለች ማለት ነው፡፡

ይህንን ነው ሊቃውንቱ ‹ሕጸጽ› (ጕድለት) ያሉት፡፡ በዚህም መሠረት ከላይ ኬክሮሱን በዓመቱ ቀናት አባዝተን ያገኘነውን 6 ዕለት ለጨረቃ ሕጸጽ ስንሰጠው የመስከረም (ጥቅምት) 1፣ የጥቅምት (ኅዳር) 2፣ የጥር (የካቲት) 3፣ የመጋቢት (ሚያዝያ) 4፣ የግንቦት (ሰኔ) 5፣ የሐምሌ (ነሐሴ) 6 ኾነው ተካፍለው ያልቃሉ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ በጨረቃና በፀሐይ ዑደት መካከል በዓመት ያለው ልዩነት 11 ቀናት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት ይኾናል፡፡ ስድስቱን ዕለታት ጨረቃ ለምታጋድልበት ሕጸጽ ብንሰጠው ቀሪ 5 ዕለት ይኖረናል፡፡ ወርኀ ጳጕሜን ማለት እነዚህ 5 ቀናት ናቸው፡፡ የዐሥራ አንዱን ዕለታት ከፈጸምን ሽርፍራፊዎቹን (15 ኬክሮስና 6 ካልዒትን) እንመልከት፤ ከላይ እንደ ተጠቀሰው በፀሐይና በጨረቃ ዓመታት መካከል የተፈጠሩትን 11 ቀናት ስድስቱ ለሕጸጽ ማሟያ ሲገቡ የቀሩት 5 ዕለታት ናቸው ጳጕሜን የምትባለውን ወር ያስገኟት፡፡

በጎርጎርዮሳውያኑ አቈጣጠር እነዚህ 5ቱ ዕለታት በጃንዋሪ፣ ማርች፣ ሜይ፣ ጁላይና ኦገስት ላይ ስለ ተጨመሩ ወሮቹ 31 ሊኾኑ ችለዋል፡፡ ይኽን የከፈለው ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በ46 ዓ.ዓ የነበረው ዩልየስ ቄሣር ነው፡፡ ዩልየስ ለአራቱ ወሮች 30 ቀን፣ ለአንዱ 28 /29 (በየአራት ዓመቱ)፣ ለቀሩት ሰባት ወሮች ደግሞ 31 ቀን ሰጥቷቸዋል፡፡ አምስቱን ወሮች 31 ያደረጋቸው ከጳጕሜን ወስዶ ሲኾን ለሁለቱ ወሮች አንዳንድ ቀን የጨመረላቸው ደግሞ ከፌቡርዋሪ (የካቲት) 2 ቀናት ወስዶ ወሩን 28 በማድረግ ነው፡፡ ከእንግዲህ የሚተርፉት ከላይ የየዕለቱን ልዩነት በዓመት ስናባዛ የቀሩት 15 ኬክሮስና 6 ካልዒት ናቸው፡፡ ሁለቱን ከላይ ያገኘናቸውን ውጤቶች ስንደምራቸው (12 ኬክሮስ + 3 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት) 15 ኬክሮስ ከ 6 ካልዒት ይመጣሉ፡፡ 1 ዕለት 60 ኬክሮስ በመኾኑ 1 ዕለትን (60 ኬክሮስን) ለማግኘት ከላይ ያገኘነውን 15 ኬክሮስ በ4 ማባዛት ይኖርብናል፡፡

በአራት ዓመት አንድ ጊዜ ጳጕሜን 6 ቀን የምትኾነውም እነዚህ በየዓመቱ የተሰባሰቡ 15 ኬክሮሶች አንድ ላይ መጥተው በአራት ዓመት አንድ ጊዜ አንድ ዕለት ስለሚኾኑ ነው፡፡ እርሷም ሠግር (leap year) ትባላለች፡፡ ጎርጎርዮሳውያኑ ይኽቺን ሠግር በፌቡርዋሪ ወር ላይ ጨምረው ወሩን በየአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ 29 ቀን ያደርጉታል፡፡ 15ቱ ኬክሮስ በአራት ዓመት ተደምረው አንድ ዕለት መጡና በአራት ዓመት አንድ ጳጕሜን ስድስት ቀን እንድትኾን አድርገዋታል፡፡ የቀረችው 6 ካልዒትስ የት ትግባ ከተባለ ካልዒት አንዲት ዕለት ትኾን ዘንድ 3600 ካልዒት ያስፈልጋሉ፡፡ ይህንን ያህል ካልዒት ለማግኘት ደግሞ 600 ዓመታት ያስፈልጉናል፡፡ ከዚኽ ስሌት አኳያ ጳጕሜን በየስድስት መቶ ዓመታት ሰባት ቀን ትኾናለች፡፡

ጳጕሜን 5 ቀን በቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ዘንድ ‹ዕለተ ምርያ› ወይም ‹የተመረጠች ቀን› ትባላለች፡፡ ሊቃውንቱ የጌታችንን ልደት ሲያሰሉባት የቆየችው ዕለት በመኾኗ ነው ይህንን ስያሜ ያገኘችው፡፡ የጌታችንን ልደት ቀን የምትወስነው የጳጕሜን 5ኛዋ ቀን ናት፡፡ በዓለ ልደት የሚውለውም ጳጕሜን 5 በዋለበት ቀን ነው፡፡ ለምሳሌ ዘንድሮ (2009 ዓ.ም) ጳጕሜን 5 ቀን እሑድ ይውላል፤ ስለዚህም በ2010 ዓ.ም የሚበረው በዓለ ልደት እሑድ ይኾናል ማለት ነው፡፡ በየአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ ጳጕሜን 6 ቀን ስትኾን ልደት በ28 የሚከበረውም በዓለ ልደት ጳጕሜን 5 ቀንን (ዕለተ ምርያን) ስለማይለቅ ነው፡፡ በዘመነ ዮሐንስ ስድስተኛዋ የጳጕሜን ቀን በዓለ ልደትን በአንድ ቀን ዝቅ ብሎ እንዲከበር ስለምታደርገው ልደትን ታኅሣሥ 28 ቀን እናከብራለን፡፡ ታድያ ምነው ጥምቀት፣ ግዝረትና ሌሎችም በዓላት አይለወጡም? ቢሉ ሊቃውንቱ የሚሰጡት ምላሽ ‹‹ትውልድ ሱባዔ እየቈጠረ በተስፋ የጠበቃት ዕለተ ልደትን ስለ ኾነ ነው፡፡ ሌሎቹ በዓላት የመጡት በልደቱ ምክንያት ነውና›› የሚል ነው፡፡

በጎርጎርዮሳውያን አቈጣጠርም በአራት ዓመት አንድ ጊዜ በዓለ ልደት ዝቅ ብሎ ይከበራል፡፡ የእነርሱ በግልጽ የማይታወቀው ጭማሪዋ ፌብርዋሪ (የካቲት) ላይ ስለምትኾን ነው፡፡ ይህ ደግሞ አዲሱን ዓመት ካከበሩ በኋላ ይመጣል፡፡ በእኛ አቈጣጠር ግን ጭማሪዋ የምትወድቀው ጳጕሜን መጨረሻ ላይ ስለ ኾነና ከአዲስ ዓመት በፊት ተደምራ ስለምትቈጠር ቍጥሯ ጐልቶ ይታወቃል፡፡ በአጠቃላይ ‹ጳጕሜን› የምትባለው አስገራሚዋና ትንሿ ወራችን እንዲህ በስሌት የተሞላች፣ በሦስት ዓመታት አምስት ቀን ኾና ቆይታ በአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ ስድስት፣ በየስድስት መቶ ዓመት ደግሞ ሰባት ቀን የምትኾን ወር ናት፡፡ እንደዚሁም ታላላቆቹ ወሮች ምንም ሳይፈጥሩ የልደትን ቀን የምትወስን፣ የዓመቱን ሠግር የምታመጣ፣ ታሪከኛ ወርም ናት፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ክረምት – ካለፈው የቀጠለ

በመጋቤ ሐዲስ ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

ነሐሴ ፳፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የተዘራው ዘር በዝናቡና በተዘራበት አፈር አማካይነት ይፈርሳል፤ ይበቅላል፤ ይለመልማል፤ ያብባል፤ ፍሬ ይሰጣል፡፡ ሰውም እንደዚሁ ነው፡፡ ይፀነሳል፤ ይወለዳል፤ ያድጋል፤ ይሞታል፡፡ ወደ መሬት ይመለሳል፤ ይፈርሳል፡፡ ትንሣኤ ዘጉባኤን ጠብቆ ይነሣል፡፡ ይህን በተመለከተ ‹‹የስንዴ ቅንጣት በምድር ወድቃ ካልሞተች ብቻዋን ትቀራለች፡፡ ብትሞት ግን ብዙ ፍሬ ታፈራለች፤›› በማለት ጌታችን አስተምሯል (ዮሐ. ፲፪፥፳፬)፡፡ ሰውም ካልሞተ አይነሣም፤ ካልተነሣም መንግሥተ ሰማያት ሊገባ አይችልምና፡፡ ምክንያቱም ግብር እምግብር ሳይለወጡ መንግሥተ ሰማያት መግባት አይቻልምና፡፡ ስለዚህ ሰው ትንሣኤ እንዳለው ገበሬ ከሚዘራው ዘር መማርና ብዙ ፍሬ ማፍራት ይጠበቅበታል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ትንሣኤ ሙታንን ባስተማረበት መልእክቱ ወርኃ ዘር የትንሣኤ ሙታን መማሪያ መኾኑን አስረድቷል፡፡ ሐዋርያው ‹‹ነገር ግን ሰው ሙታን እንዴት ይነሣሉ? በምንስ አይነት አካል ይመጣሉ? የሚል ይኖር ይኾናል፡፡ አንተ ሞኝ፣ የቆሮንቶስ ገበሬ አንተ የዘራኸው ካልሞተ ሕያው አይኾንም፡፡ የምትዘራውም ስንዴ ቢኾን ከሌላም ዓይነት (በቆሎ፣ ኑግ) የአንዱ ቢኾን ቅንጣት (ፍሬ) ብቻ ነው እንጂ የምትዘራው የሚኾነውን አካል አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ግን እንደ ወደደ አካልን ይሰጠዋል፤›› በማለት አስተምሯል (፩ኛ ቆሮ. ፲፭፥፴፭)፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ተናገረው የሰው ልጅ እንደ ዘር በመበስበስ ይዘራል፤ በአለመበስበስ ይነሣል፡፡ በውርደት (አራት አምስት ሰው ተሸክሞት) ይዘራል፤ ይቀበራል፤ በክብር ይነሣል፡፡ በድካም ይዘራል፤ በኀይል ይነሣል፡፡ በፍጥረታዊ አካል ይዘራል፤ ሟች፣ ፈራሽ፣ በስባሽ አካል ይቀበራል፡፡ በመንፈሳዊ አካል ይነሣል ማለት የማይሞት፣ የማይታመም፣ የማይደክም ኾኖ ይነሣል ማለት ነው፡፡ ከዚህ ላይ አንድ ገበሬ ስንዴ ከዘራ ስንዴ፣ ጤፍ ከዘራ ደግሞ ጤፍ፣ በቆሎም ከዘራ በቆሎ፣ ኑግ ቢዘራ ኑግ እንደሚኾን አካሉን ለውጦ እንደማይበቅል ሰውም የራሱን ማንነት ይዞ የሚነሣ መኾኑንም ጭምር ነው ያስተማረን፡፡ ሰው ክፉ የሠራም፣ ጽድቅ የሠራም የራሱን ሥራ ይዞ ይነሣል እንጂ ጻድቁ ኀጥእ ኀጥኡ ጻድቅ ኾኖ አይነሣም፡፡ እንደ ሥራው ዋጋውን የሚቀበልበት ነውና፡፡ ‹‹ሰው የዘራውን ያጭዳል›› እንዲል (ገላ. ፮፥፯)፡፡ በሌላ አንቀጽ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፤ ‹‹በጥቂት የሚዘራ በጥቂት ያጭዳል፤ በበረከትም የሚዘራ ደግሞ በበረከት ያጭዳል፤›› (፪ኛ ቆሮ. ፱፥፮)፡፡ ይህንም ስለ መስጠትና መቀበል አስተምሮታል፡፡ የዘራ እንደሚሰበስብ፣ የሰጠም ዋጋውን አያጣምና የተዘራባት ምድር የዘሩባት አብዝታ እንደምትሰጥ፣ በምጽዋት መልክ የተቀበሉ ነዳነያንም ትልቅ ዋጋ ያሰጣሉና በሚያልፍ የማያልፍ፤ በሚያልቅ የማያልቅ ዋጋ ያስገኛሉና፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ምጽዋትን በዘር መስሎታል፡፡ ‹‹ዘርን ለዘሪ፣ ለመብላትም እንጀራን በብዙ የሚሰጥ እርሱም የምትዘሩትን ዘር ይሰጣችኋል፤›› እንዲል (፪ኛ ቆሮ. ፱፥፲)፡፡

‹‹ብዙ ጊዜ በእርሷ ላይ የሚወርደውን ዝናም የምትጠጣ መሬት ለሚያርሷትም ደግሞ የምትጠቅምን አትክልት የምታበቅል ከእግዚአብሔር በረከትን ታገኛለችና፡፡ እሾኽንና ኩርንችትን ግን ብታወጣ የተጣለች ናት፡፡ ለመርገምም ትቀርባለች መጨረሻዋ መቃጠል ነው፤›› (ዕብ. ፮፥፯) ተብሎ እንደ ተጻፈ መሬት የተባለ የሰው ልጅ፤ ዘር የተባለ ደግሞ ቃለ እግዚአብሔር ነው፡፡ ዝናም የተባለ ትምህርት፤ እሾኽ የተባለ ኀጢአት፣ ክፋት ነው፡፡ ምድር የዘሩባትን ባታበቅል መጨረሻዋ መቃጠል እንደ ኾነ ዅሉ የሰው ልጅም አደራውን ባይጠብቅ፣ የንስሐ ፍሬ ባያፈራ ፍጻሜው መከራ ይኾናል፡፡ ሰው እንደ ዘር ወደ መሬት እንደሚመለስ ዘሩ ፈርሶ፣ በስብሶ ከበቀለ በኋላ ፍሬ እንደሚሰጥ ሰውም ከሞተ በኋላ ትንሣኤ ያለው መኾኑን በማሰብ መልካም ሥራን መሥራት ይገባናል፡፡ ከዚህ አለፍ ብለን ዘር የሚለውን ቃል ስንመለከተው ድንቅ ምሥጢር ያዘለ መኾኑን እንገነዘባለን፡፡ ‹‹የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ዘርን ባያስቀርልን ኖሮ እንደ ሰዶም በኾንን፤ ገሞራንም በመሰልን ነበር፤›› እንዳለ (ኢሳ. ፩፥፱)፡፡ ይህም እኛን ለማዳን ከእናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደውን ክርስቶስን ያመላክታል፡፡ ‹‹የነሣውን ሥጋ ከመላእክት የነሣው አይደለም፡፡ ከአብርሃም ዘር ነው እንጂ፤›› እንዲል (ዕብ. ፪፥፲፮)፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ይህ ዘር ምን ያህል ታላቅ መኾኑን ሲያስረዳ ‹‹ዳግመኛ የተወለዳችሁት ከሚጠፋ ዘር አይደለም፤ በሕያውና ለዘለዓለም በእግዚአብሔር ቃል ከማይጠፋ ዘር ነው እንጂ፤›› (፩ኛ ጴጥ. ፩፥፳፫)፡፡ የማይጠፋ ዘር የተባለውም ክርስቶስ ነው፡፡ ከእርሱ ተወልደናልና እርሱንም በመከራው መስለነው በትንሣኤውም ልንመስለው ያስፈልጋል፡፡

፫. ክረምት ወርኃ ልምላሜ ነው

በክረምት ወቅት ከዘር ተከትሎ ምድር በቅጠል በልዩ ልዩ የልምላሜ ዓይነቶች አሸብርቃ፣ ደምቃ በዋዕየ ፀሐይ የተራቆተ ማንነቷ በቅጠል የሚሸፈንበት ወቅት ነው፡፡ በመኾኑም ወቅ ወርኃ ልምላሜ ነው፡፡ ፍሬ ግን የለም፤ ይህን ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ ‹‹ሰማይን በደመና ይሸፍናል፤ ለምድርም ዝናምን ያዘጋጃል፡፡ ሣርን በተራሮች ላይ ያበቅላል፤ ለምለሙንም ለሰው ልጆች ጥቅም፡፡ ለሚጠሩት ለቍራ ጫጩቶች ለእንስሶችም ምግባቸውን ይሰጣል፤›› (መዝ. ፻፵፮፥፰-፲) በማለት ወቅቱ የልምላሜ፣ የሣርና የቅጠል፤ እንስሳት ሣር ቅጠሉን ከማንኛውም ጊዜ በበለጠ የሚያገኙበት ወቅት እንደ ኾነ ገልጿል፡፡ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው በቢታንያ መንገድ ላይ በተራበ ጊዜ ያያት በለስ ቅጠል ብቻ እንደ ነበረች፤ ጌታችንም ‹‹ለዘለዓለሙ ፍሬ አይገኝብሽ›› ብሎ እንደ ረገማት፤ በለሲቱም ወዲያውኑ እንደ ደረቀች በወንጌል ተጽፏል (ማቴ. ፳፩፥፲፰)፡፡ ያ ጊዜ የክረምት ወቅት (የቅጠል ወቅት) ነበር፡፡ ይህም በነቢያት ዘመን ይመሰላል፡፡ በዘመነ ነቢያት ዅሉም በተስፋ ብቻ ይኖሩ ነበር፡፡ ‹‹ብዙ ነቢያትና ጻድቃን ሊያዩ ተመኙ፤ አላዩም፡፡ የምትሰሙትን ሊሰሙ ተመኝተው አልሰሙም፤›› እንዳለ ጌታችን (ማቴ. ፲፫፥፲፮)፡፡ ገበሬውም የዘራውን ዘር መብቀል በተስፋ እየተመለከተ፣ አረሙን እየነቀለ፣ ዙሪያውን እያጠረ፣ እየተንከባከበ ይጠብቃል፡፡ ደግሞም ፈጣሪውን ከበረድ እንዲጠብቅለት እየተማጸነ የራት ሰዓት እስኪደርስ መቆያ እንዲቀምስ ይህ ቅጠል ፍሬ እስኪሰጥም በተስፋ አለኝ እያለ ቅጠሉን የዐይን ምግብ አድርጎ ይጠባበቃል፡፡

በሌላ መልኩ የእግዚአብሔር መንግሥት ዘሪ በእርሻው ላይ የዘራውን ዘር እንደምትመስል ተጽፏል፡፡ ‹‹በምድር ዘርን እንደሚዘራ ሰው የእግዚአብሔር መንግሥት እንዲህ ናት፡፡ ሌሊት ይተኛል፤ ቀን ይነሣል፡፡ እርሱም (ገበሬው) እንዴት እንደሚኾን ሳያውቅ ዘሩ ይበቅላል፤ ያድግማል፡፡ ምድሪቱም አውቃ በመጀመሪያ ቡቃያ፣ ኋላም ዛላ፣ በዘለላው ፍጹም ፍሬ ታፈራለች፡፡ ፍሬው ሲበስል መከር ደርሷልና ወዲያው ማጭድ ይልካል፤›› እንዳለ (ማር. ፬፥፳፮-፳፱)፡፡ በገበሬ የተመሰለው ኢየሱስ ክርስቶስም እኛ በዓለም ላይ ያለን የሰው ዘሮች በሙሉ በመከር ያፈራውም ያላፈራውም እንደሚሰበሰብ ያሳየናል፡፡ ‹‹እንግዲህ ወንድሞች ሆይ፣ ጌታ እስኪመጣ ድረስ እነሆ ገበሬው የፊተኛውን፣ የኋለኛውን ዝናም እርሱን የታገሠ የከበረውን የምድር ፍሬ ይጠብቃል፡፡ እናንተም ደግሞ ታገሡ፤›› እንዳለ ሐዋርያው (ያዕ. ፭፥፯-፱)፡፡ ገበሬ ቅጠሉ ፍሬ እስከሚሰጥ ምን ያህል መከራን እንደሚታገሥ እኛም መንግሥተ ሰማያት ለመግባት ቅጠል ብቻ የኾነ ማንነታችን የንስሐ ፍሬ እስኪያፈራ ድረስ መከራውን መታገሥ ይገባናል፡፡ ምድራዊ ፍሬ ለማግኘት ይህን ያህል መጠበቅና መታገሥ ካስፈለገ ሰማያዊ ዋጋ ለመቀበል ምን ያህል መታገሥ ያስፈልግ ይኾን? ከወርኃ ቅጠል ያለ ፍሬ ብንገኝ መርገምን እንደምናተርፍ፣ ብናፈራ ግን ገበሬ ምርቱን ደስ ብሎት እንዲሰበስብ ፈጣሪያችንም በእኛ እንደሚደሰትና ዋጋችንን እንደሚሰጠን እንማራለን፡፡ ክረምት ጥልቅ ትምህርት የምንማርበት እግዚአብሔር በሰፊው የሚገለጽበት ወቅት ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡