የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መገናኛ ብዙኃን አገልግሎት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ኅዳር ፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመገናኛ ብዙኃን አገልግሎት ድርጅት አቋቁማ መደበኛ የሃያ አራት ሰዓት የቴሌቭዥን መርሐ ግብር ከጀመረች ከሁለት ዓመታት በላይ ተቈጥረዋል፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን፣ የቴሌቭዥን ሥርጭቱን አጀማመርና ጠቅላላ አገልግሎት በአጭሩ የሚያስቃኝ ጽሑፍ ይዘን ቀርበናል፡፡ መልካም ንባብ ይኹንላችሁ!

በቤተ ክርስቲያናችንና በአገራችን ታሪክ እንደሚታወቀው ያልተበረዘና ያልተከለሰ ኦርቶዶክሳዊ ዶግማና ሥርዓተ አምልኮ፣ የትርጓሜና የባሕረ ሐሳብ ትምህርት፣ በብራና የተጻፉ ቅዱሳት መጻሕፍት፣ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት፣ መሥዋዕተ ኦሪት ይቀርብባቸው የነበሩና እስከ አሁን ድረስ ተጠብቀው የቆዩ ጥንታውያን አድባራትና ገዳማት፣ የቅዱስ ያሬድ የዜማ ድርሰቶች፣ ሥርዓተ ማኅሌትና የመንፈሳውያን በዓላት አከባበር ሥርዓት፣ ወዘተ. የመሳሰሉ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ ቅርሶች በሙሉ ዓለምን የሚያስደምሙ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሀብቶችና ልዩ ስጦታዎች ናቸው፡፡

ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ በመጽሐፋቸው እንደ ጠቀሱት ሙሉ ትምህርት፣ ፍጹም ቋንቋ ከነፊደሉ፣ ሥነ ጥበብ፣ ሥነ ጽሑፍ፣ ኪነ ጥበብ፣ ታሪካዊና ጥንታዊ ቅርስ፣ እምነት፣ ነጻነት፣ አንድነት፣ የአገር ፍቅር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለኢትዮጵያ ሕዝብ ካበረከተቻቸው ብዙ ስጦታዎች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ እንደ ብፁዕነታቸው ማብራሪያ አሁንም ቢኾን ትውልዱ ጀግንነትን፤ አገር ወዳድነትን፤ ለሃይማኖት፣ ለታሪክና ለባህል ተቆርቋሪነትን ይዞ እንዲያድግ በማስተማርና በማበረታታት ረገድ ቤተ ክርስቲያን ድርሻ አላት (የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ)፡፡

በረከታቸው ይደርብንና ካሁን በፊት በየጊዜው የተነሡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በቃል በማስተማርና መጻሕፍትን በማሳተም እነዚህን ሀብቶቿን ለመጠበቅና ለዓለም ለማስተዋወቅ ያደረጉት አስተዋጽዖ ከፍተኛ ነው፡፡ ከኅትመት ውጤቶች ባሻገርም መገናኛ ብዙኃንን በመጠቀም ቃለ እግዚአብሔር ለማስተማር ቀደምት የቤተ ክርስቲያን አባቶች ብዙ ደክመዋል፡፡ ለዚህም በአሁኑ ሰዓት አገልግሎት ባይሰጥም ቀደም ሲል የተጀመረው የሬድዮ መርሐ ግብር እንደዚሁም አሁንም አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኙት መንፈሳዊ መጽሔቶች፣ ጋዜጦችና ድረ ገጾች ማስረጃዎች ናቸው፡፡ መገናኛ ብዙኃንን በተለይም የቴሌቭዥን ሥርጭትን በመጠቀም ረገድ እንደ ግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ያሉ አኃት አብያተ ክርስቲያናት ተሞክሮ በምሳሌነት የሚጠቀስ ነው፡፡

ብዙ ጊዜ እንደሚነገረው በሁለት ቋንቋዎች ብቻ የሚግባቡና በቍጥር ከዐሥር ሚሊዮን የማይበልጡ ምእመናን የሚገኙባት የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከዐሥር በላይ የቴሌቭዥን ጣቢያዎችን በመክፈት ትምህርተ ወንጌልን በመላው ዓለም በማዳረስ ላይ ትገኛለች፡፡ በምእመናን ብዛት ከኢትዮጵያ ብዙ እጥፍ የምታንሰዋ ግብጽ በዚህ መልኩ የመገናኛ ብዙኃን ተጠቃሚ ከኾነች ከሰማንያ በላይ ቋንቋዎችን የሚናገሩና ወደ አምሳ ሚሊዮን የሚደርሱ ምእመናን ባለቤት ለኾነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አንድ ብቻ ሳይኾን በርካታ የቴሌቭዥን ጣቢያዎች እንደሚያስፈልጓት አያጠያይቅም፡፡ ይህን እውነት ከግምት ውስጥ በማስገባት ቅዱስ ሲኖዶስ ባሳለፈው ውሳኔ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከዓመታት በፊት የሃያ አራት ሰዓት የቴሌቭዥን መርሐ ግብር ማሠራጨት ጀምራለች፡፡

በ፳፻፱ ዓ.ም በታተመው ዐዋጅ ነጋሪ መጽሔት እንደ ተገለጸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመገናኛ ብዙኃን አገልግሎት ድርጅት እንዲቋቋም ለማድረግ ጥናት እንዲካሔድ ለመጀመሪያ ጊዜ የተወሰነው በጥቅምት ወር ፳፻፮ ዓ.ም የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ነው፡፡ በዚያው ዓመት በግንቦት ወር በተካሔደው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ፤ ሦስት ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ በርካታ ባለሙያዎችና ሊቃውንት የተሳተፉበት ጥናት ለምልዓተ ጉባኤው ቀርቦ የድርጅቱ መተዳደሪያ ደንብ፣ የአርትዖትና የቴክኒክ መመሪያ ጸድቆ ሥራው እንዲጀመር ተወስኗል፡፡

ድርጅቱ፣ በቋሚ ሲኖዶስ በተሰየመው የቦርድ ሥራ አመራር ከአንድ ዓመት በላይ ተጨማሪ ጥናቶችን ሲያደርግ ቆይቶ በጥቅምት ወር ፳፻፰ ዓ.ም ለሥራው የሚያስፈልገው በጀት በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ተወስኖለታል፡፡ ቦርዱ የተፈቀደውን በጀትና የተጠናውን ጥናት ወደ ተግባር ለመለወጥ ውድድር በማድረግ ለድርጅቱ ሥራ አስኪያጅ እንዲቀጠር አድርጓል፡፡ በቅዱስ ሲኖዶስ በጸደቀው የድርጅቱ መተዳደሪያ ደንብ መሠረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመገናኛ ብዙኃን አገልግሎት ድርጅት ዋና መሥሪያ ቤት በጠቅላይ ጽ/ቤቱ ግቢ ውስጥ ይገኛል፡፡

በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት አባታዊ መመሪያ ሰጭነት አስፈላጊ ቅድመ ኹኔታዎችን በሟሟላት፣ ተደጋጋሚ ውይይቶችንና ዓለም አቀፍ ዳሰሳዎችን በማድረግ ለሥርጭቱ ያመነበትን የሳተላይት ጣቢያ አወዳድሮ በመምረጥና የውል ስምምነት በማዘጋጀት በአፋጣኝ የሥርጭት አገልግሎቱን ጀምሯል፡፡ በኢየሩሳሌም ከሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማት ጋር በተደረገ ስምምነት መሠረትም የቴሌቭዥን መርሐ ግብራቱ በአገር ውስጥ ተዘጋጅተው ኢየሩሳሌም በሚገኘው የሳተላይት ድርጅት አማካይነት ይሠራጫሉ፡፡ የቴሌቭዥን ጣቢያው የሥርጭት አድራሻም የሚከተለው ነው፤

Ethiopian Orthodox Tewahedo Church Television (EOTC TV)

Satellite: Eutelsat/Nilesat (ኢትዮጵያ)

Frequency …. 11353 (5) Vertical

Symbol rate …. 27500/FEC…5/6

Satellite: Galaxy 19 (G-19) (ሰሜን አሜሪካ)

Frequency …. 11960/Vertical

Symbol rate …. 22000/FEC…3/4

የድርጅቱ መዋቅርና አገልግሎት የተሟላ እንዲኾን በአስተዳደርና ፋይናንስ፣ በመርሐ ግብር ዝግጅት እና በቴክኒክ ዘርፍ ቦርዱ በሰየማቸው የቅጥርና የምዘና ኮሚቴ አባላት አስፈጻሚነት የሠራተኞች የቅጥር ሒደት ተከናውኗል፡፡ በቅጥር ሒደቱም ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት በወጣው ማስታወቂያ መሠረት ላመለከቱ ሠራተኞችና ለቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ቅድሚያ ተሰጥቷል፡፡ የሥርጭቱን አጠቃላይ ይዘትና ዓይነት በተመለከተም ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የቦርድ አባላትና የሚዲያ ባለሙያዎች የሚገኙበት የይዘትና የዓይነት ዝግጅት ኮሚቴ ተዋቅሯል፡፡ ይዘቱንና ዓይነቱን የሚያርምና የሚገመግም የኤዲቶሪያል ኮሚቴም ተቋቁሟል፡፡ የኤዲቶሪያል ኮሚቴው አባላትም በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪጁ የተሰየሙና በቦርዱ የተመረጡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ናቸው፡፡ ድርጅቱ ካለበት ሠፊ ሥራና ከባድ ሓላፊነት አኳያ በቋሚነት የሚያስፈልጉት በርከት ያሉ ስቱዲዮዎች፣ የቅድመ ሥርጭትና ድኅረ ሥርጭት ተግባራት ማከናወኛነት የሚያገለግሉ በርካታ ክፍሎች፣ አብያተ መዛግብት፣ አስተዳደርና የባለሙዎች ቢሮዎች እንዲሟሉ ለማድረግ ድርጅቱ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤትና ከሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ አባቶች መመሪያን በመቀበል በመሥራት ላይ ይገኛል፡፡

(ምንጭ፡- ዐዋጅ ነጋሪ መጽሔት፣ ፱ኛ ዓመት፣ ቍጥር ፲፪፤ ጥቅምት ፳፻፱ ዓ.ም፣ ገጽ 77-78)፡፡

ጽሑፋችንን ለማጠቃለል ያኽል፣ የሥልጣኔ ውጤቶች በተበራከቱበትና አብዛኞቹ ወጣቶች ዓለማዊ መልእክት በሚያስተላልፉ መገናኛ ብዙኃን ተጽዕኖ ውስጥ በወደቁበት በአሁኑ ዘመን ወጣቱን ትውልድ ወደ ጥፋት ከሚወስዱ መልእክቶች ለመታደግ ያመች ዘንድ ትምህርተ ወንጌልን ለማዳረስና ኦርቶዶክሳዊ ሕይወትን ለማስተማር፤ የቤተ ክርስቲያናችንን ሥርዓተ እምነት፣ ትውፊትና ልዩ ልዩ ሀብቷን ወይም የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ ቅርሶቿን ለትውልድ ለማቆየት ብሎም ለዓለም ለማስተዋወቅ፤ እንደዚሁም በየጊዜው በቅዱስ ሲኖዶስ የሚወጡ መመሪያዎችንና መልእክቶችን በአፋጣኝ ወደ ሕዝበ ክርስቲያኑ ለማስተላለፍ መገናኛ ብዙኃንን፣ ከመገናኛ ብዙኃንም የቴሌቭዥን ሥርጭትን መጠቀም ከፍተኛ ጠቀሜታ አለው፡፡

በዚህ ዓላማ መሠረት የተጀመረው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቴሌቭዥን ሥርጭትም በልዩ ልዩ ዓምዶቹ ትምህርተ ወንጌል በመስጠት፤ ቅዱሳት መካናትን፣ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ የቤተ ክርስቲያን ቅርሶችን በማስተዋወቅ፤ ጠቃሚ የኾኑ ማኅበራዊና ወቅታዊ ጉዳዮችን በማቅረብና መንፈሳዊ ዜናዎችን በመዘገብ አገልግሎቱን እንደ ቀጠለ ነው፡፡ የቴሌቭዥን ሥርጭቱን በተቀላጠፈ መልኩ ለማስቀጠልና ለምእመናን ለማዳረስ ይቻል ዘንድም መላው ሕዝበ ክርስቲያን ሐሳብ አስተያየት በመስጠትና በሌላም ልዩ ልዩ መንገድ በተቻለን አቅም ዂሉ የቤተ ክርስቲያናችንን የመገናኛ ብዙኃን አገልግሎት ድርጅት በመደገፍ የሚጠበቅብንን ክርስቲያናዊ ሓላፊነት እንወጣ ሲል የማኅበረ ቅዱሳን አማርኛ ድረ ገጽ ዝግጅት ክፍል መንፈሳዊ መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ዘመነ ጽጌ

በዶክተር ታደለ ገድሌ

ጥቅምት ፳፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓተ አምልኮ መሠረት ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፭ ቀን ያለው ወቅት ‹ዘመነ ጽጌ፤ ወርኀ ጽጌ› ተብሎ ይጠራል፡፡ በግእዝ ቋንቋ ‹ጸገየ› ማለት ‹አበበ፤ አፈራ፤ በውበት ተንቆጠቆጠ፤ በደም ግባት አጌጠ፤ የፍሬ ምልክት አሣየ› እንደ ማለት ነው፡፡ ከዚሁ ግስ ላይ ‹ጽጌያት› ብሎ ስም ማውጣት ሲቻል አበባማ፣ ውበታማ፣ አበባ የያዘና የተሸከመ ለማለት ደግሞ ‹ጽጉይ› ይላል፡፡ በተለይም ዘመነ ጽጌ (ወርኀ ጽጌ) የምትከበረው በሀገራችን ከወቅቶች ሁሉ በጣም በሚወደደው የመፀው ወቅት ነው፡፡ በዚህ ምድር በልምላሜና በውበት በምትንቆጠቆጥበት ወቅት በየሳምንቱ እሑድ ከመንፈቀ ሌሊት ጀምሮ ማኅሌተ ጽጌ የሚቆሙትና ሰዓታት የሚያደርሱት ካህናት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በአበባ፣ በትርንጎ፣ በሮማን፣ በእንጆሪ … እየመሰሉ ለፈጣሪ መዝሙርና ምስጋና ያቀርባሉ፡፡

በዘመነ ጽጌ ‹‹ጊዜ ገሚድ በጽሐ ቃለ ማዕነቅ ተሰምዓ በምድርነ፤ ተመየጢ ተመየጢ ወንርዓይ ብኪ ሰላመ፤ እንዘ ተሐቅፊዮ ለሕፃንኪ፤ ክበበ ጌራ ወርቅ ጽሩይ በዕንቈ ባሕርይ ዘየኀቱ፤ አክሊለ ጽጌ ማርያም፤ ንዒ ርግብየ ወንዒ ሠናይትየ፤ እንተ ሐዋርያት ይሴብሑኪ መላእክት ይትለአኩኪ፤ ንዒ እምሊባኖስ ሥነ ሕይወት፤ ቡራኬሁ ለሴም፤ ተናግዶቱ ለአብርሃም መዓዛሁ ለይስሐቅ ወሰዋስዊሁ ለያዕቆብ ወናዛዚቱ ለዮሴፍ …›› ይህን የመሳሰሉ ኃይለ ቃላትን እያነሡ ሊቃውንቱና ምእመናኑ እግዚአብሔርንና እመቤታችንን ያመሰግናሉ፡፡

ይህም ማለት ‹‹… በአበባው ወቅት መሆን የሚገባው ነገር ሁሉ ደረሰ፡፡ የአዕዋፍ ውዳሴ ቃልም በምድራችን ተሰማ፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሆይ! በአንቺ ሰላምን ማየት እንችል ዘንድ መመለስን ተመለሺ፡፡ ልጅሽን እንዳቀፍሽ፤ ክበቡ ያማረ ወርቅ እንደ ተጎናጸፍሽ የአበባ አክሊል ማርያም ርግቤ፣ ደጌ ሆይ! ነይ፡፡ ሐዋርያት የሚያመሰግኑሽ፤ መላእክት የሚላላኩሽ፤ የሕይወት መሠረት ከሊባኖስ ነይ፡፡ የሴም በረከቱ፤ የአብርሃም መስተንግዶው፤ የይስሐቅ ሽቶው፤ የያዕቆብ መሰላሉ፤ የዮሴፍ አጽናኙ …›› በሚሉና በሌሎችም የዜማ ስልቶች ካህናትና ዲያቆናት፤ ደባትር (ደብተሮች) በቅኔ ማኅሌት ውስጥ ጧፍ እያበሩና እየዘመሩ፤ ከበሮ እየመቱ፤ ጸናጽል እያንሹዋሹ፤ በመቋሚያ አየሩን እየቀዘፉና መሬቱን እየረገጡ፤ እየወረቡ ሌሊቱን ሙሉ ለእግዚአብሔር ምስጋና ያቀርባሉ፡፡

ሰዓታት የሚያደርሱ ካህናትም፡- ‹‹ትመስሊ ምሥራቀ፤ ወትወልዲ መብረቀ፤ ወታገምሪ ረቂቀ፡፡ ትመስሊ ፊደለ፤ ወትወልዲ ወንጌለ፤ ወታገምሪ ነበልባለ፡፡ ትመስሊ ጽጌ ረዳ፤ ወትወልዲ እንግዳ፤ ወታድኅኒ እሞተ ፍዳ … ሐረገ ወይን ሐረገ ወይን ዐፀደ ወይን አንቲ ማርያም›› ማለት፡- ‹‹በምሥራቀ ፀሐይ የምትመሰየሚው፤ እንደ መብረቅ ኃያል የሆነውን ጌታን የወለድሽ፤ ረቂቅ ምሥጢርን የምትችዪ፤ እንደ ፊደል ባለ ብዙ ዘር (ሆሄያት) የሆንሽ፤ ወንጌልን የወለድሽ፤ ነበልባለ እሳትን (ክርስቶስን) የተሸከምሽ፤ በጽጌ ረዳ አምሳል የምትመሰየሚው ቅድስት ማርያም ሆይ! የዓለሙን እንግዳ ፈጣሪን የወለድሽ፤ ከፍዳ ሞት የምታድኚ፤ የወይን ሐረግ የወይን ዐፀድ (ተክል) አንቺ ነሽ …›› እያሉ ያመሰግናሉ፡፡

‹‹እምግብጽ ጸዋዕክዎ ለወልድየ ለክብረ ቅዱሳን፤ ለቅዱሳን ክብር ልጄን ከግብጽ ጠራሁት›› በማለት ነቢዩ ሆሴዕ በምዕራፍ ፲፩ ቍጥር ፩ እና ፪ ላይ አስቀድሞ እንደ ተናገረው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በልጅነቱ ወደ ምድረ ግብጽ (ምስር) የተሰደደው የነቢያት ትንቢት ይፈጽም ዘንድ ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ሕፃናትን በመፍጀት ከሚታወቀው ከአረመኔው ንጉሥ ከሄሮድስ ለማምለጥ ነው፡፡ አምላካችን ክርስቶስ ያለጊዜው (ዕለተ ዓርብ) ደሙ አይፈስምና፡፡ ስለዚህም ‹‹ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ ምድረ ግብጽ ሽሽ፤ ሄሮድስ ሕፃኑን ለመግደል ይፈልጋልና›› ብሎ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ለዮሴፍ በነገረው ቃል መሠረት ሕፃኑንና እናቱን ይዞ በሌሊት ወደ ግብጽ ምድር ተሰደደ፡፡ ይህንን ስደት አስመልክቶ ሰቆቃወ ድንግል የሚባለውን ቃለ እግዚአብሔር ካህናቱ በሚያሳዝን ዜማ ያደርሳሉ፤ ያቀርባሉ፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በይሁዳ ግዛት በቤተልሔም በንጉሥ ሄሮድስ ዘመን በተወለደ ጊዜ በሄሮድስ ላይ ቅንዓት አድሮበት ነበር፡፡ ‹‹ከአንተ የሚበልጥና የሚልቅ ንጉሥ በቤተልሔም ይወለዳል›› የሚል ትንቢት ይሰማ ነበር፡፡ ‹‹ወአንቲነ ቤተ ልሔም ምድረ ኤፍራታ ኢትቴሐቲ እምነገሥተ ይሁዳ እስመ እምኔኪ ይወፅዕ ንጉሥ፤ አንቺ የኤፍራታ ምድር ቤተልሔም ሆይ! ብዙ ነገሥታት ከነገሡባት ከይሁዳ አታንሺም፤ የዓለም ንጉሥ የሚሆን ከአንቺ ይወጣልና›› የሚለው የነቢያት ትንቢት ሄሮድስን አስጨነቀው፡፡ በዚህ ላይ ደግሞ ሰብአ ሰገል (የጥበብ ሰዎች) ‹‹የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ የት አለ? የምሥራቅ ኮከብ እየመራን መጥተናል፡፡ እንሰግድለት ዘንድ አመላክቱን›› ብለው ወደ ኢየሩሳሌም ብዙ መብዓ ይዘው መምጣታቸውን ሄሮድስ ሲሰማ ዓይኑ ፈጠጠ፤ ሰውነቱም ደነገጠ፡፡ ስለዚህም ጌታችንን ሊገድለው ወደደ፡፡

ለሥልጣን ስሱ የነበረው ሄሮድስ ‹‹ከእኔ በላይ ሌላ ምን ንጉሥ አለ?›› ብሎ ተቆጣና የካህናትን አለቆችና የሕዝቡን ጻፎች (ፈሪሳውያንን) አስጠርቶ በመሰብሰብ ‹‹ክርስቶስ የተወለደው የት ነው?›› ብሎ አፈጠጠባቸው፡፡ በኋላም አንደበቱን አለሰለሰና ‹‹እውነት ከሆነ እኔም እሰግድለት ዘንድ ፈልጉልኝ›› አለ ብልጡ ንጉሥ፡፡ ካህናቱም ከልቡ መስሏቸው ‹‹‹አንቺ ቤተልሔም የይሁዳ ምድር ከይሁዳ ገዢዎች ከቶ አታንሽም፤ ሕዝቤን እስራኤልን የሚጠብቅ መስፍን ከአንቺ ይወጣልና› ተብሎ በተጻፈው መሠረት ጌታችን የተወለደው በይሁዳ በቤተልሔም ነው፡፡ ሰብአ ሰገልም አምኃ (እጅ መንሻ) ለማቅረብ የሚሔዱት ወደዚያው ነው›› ብለው እቅጩን ነገሩት፡፡ ሄሮድስም መንገደኞቹን ሰብአ ሰገልን ጠራና ‹‹ወገኖቼ አደራችሁን ለተወለደው ልጅ መብዓ አድርሳችሁ በእኔ በኩል ተመለሱ፡፡ እኔ ደግሞ ሒጄ እሰግድለት ዘንድ ሁኔታውን ትነግሩኛላችሁ›› ብሎ አሰናበታቸው፡፡

እነርሱም ‹‹ኧረ ግድ የለም ንጉሥ ሆይ!›› ብለው የምሥራቁ ኮከብ እየመራቸው፤ ሕፃኑ ባለበት ቦታ ላይ ደርሰው፤ ወደ ቤትም ገብተው፤ ወድቀው ለሕፃኑ ሰገዱለት፡፡ ሳጥኖቻቸውንም ከፍተው እጅ መንሻ ወርቅና ዕጣን፣ ከርቤም አቀረቡለት፡፡ ሲመለሱ በሌላ መንገድ እንዲሔዱ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በሕልም ነግሯቸው ነበርና በሌላ መንገድ ወደ ሀገራቸው ተጓዙ፡፡ ሄሮድስ ይህን በመሰማ ጊዜም የበለጠ ቅንዓት አደረበትና ሕፃኑን ለመግደል ይበልጥ ተነሣሣ፡፡ በሐሳብ የተጨነቀው ንጉሥ ጉዳዩን ለመጠንቁል (ለጠንቋይ) አማከረ፡፡ ጠንቋይ መቼም እበላና እወደድ ባይ ነውና ‹‹‹እስከ ሁለትና ሦስት ዓመት ዕድሜ ለአላቸው ወንድ ሕፃናት ቀለብ ልሠፍርላቸው አስቤአለሁና ተሰብሰቡ› ብለው አዋጅ ያስነግሩ፡፡ ሕፃናቱን ሲሰበሰቡልዎም ያን ጊዜ ሁሉንም ይግደሏቸው፡፡ ከዚያ ውስጥ የእርስዎ የወደፊት ጠላት አብሮ ይሞታል›› ብሎ መከረው፡፡ በዚህ መሠረት በመቶ ሺሕ የሚቆጠሩ ሕፃናትን ሄሮድስ አስፈጅቷል፡፡ ‹‹ድምፅ በራማ ተሰማ፤ ለቅሶና ብዙ ዋይታ፡፡ ራሔል ስለ ልጆቿ አለቀሰች፡፡ መጽናናትም አልወደደችም፤ የሉምና›› የሚለው ትንቢትም ተፈጸመ፡፡

ከሦስት ዓመት ከመንፈቅ የግብጽ ስደት በኋላ ሊቃውንቱ፡- ‹‹ተመየጢ ማርያም ሀገረኪ ናዝሬተ፣ በላዕሌኪ አልቦ ዘያበጽሕ ሁከተ፣ ወኢትጎንድዪ በግብጽ ከመ ዘአልብኪ ቤተ፣ ዘየኀሥሦ ለወልድኪ ይእዜሰ ሞተ፣ በከመ ነገሮ መልአክ ለዮሴፍ ብሥራተ›› እያሉ ከስደት መመለሷን ያበሥራሉ፡፡ ትርጉሙም፡- ‹‹ማርያም ሆይ! ወደ ሀገርሽ ወደ ናዝሬት ተመለሺ፡፡ በአንቺ ላይ ሁከት የሚያመጣ ማንም የለም፡፡ ቤት እንደሌለሽ ሁሉ በግብጽ አትቆይ፡፡ ለዮሴፍ በሕልሙ መልአክ እንደ ነገረው የሕፃኑን ነፍስ የፈለገው (ጠላት ሄሮድስ) ሞቷልና›› ማለት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን በዐርባው ቀን (በዘመነ ጽጌ) ወቅት የማርያምን የሽሽትና የመመለስ (የሚጠት) ታሪክ እያነሡ ውዳሴ የሚያቀርቡትና ማኅሌት የሚቆሙት በዚሁ ምክንያት ነው፡፡ በዚህ ወቅት ለእመቤታችን ክብር ሲባል የፈቃድ ጾም የሚጾሙ ምዕመናንና ምዕመናትም ብዙዎች ናቸው፡፡

መምህር ክፍሌ ወልደ ጻድቅ ‹የጽጌ ዚቅ› በሚለው፣ ዓመተ ምሕረት በሌለውና በእጅ ጽሑፍ ተዘጋጅቶ በታተመው መጽሐፋቸው ከገጽ 1 – 75 እንደ ገለጹት ከበዓለ ጽጌ ጋር የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፤ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፤ የቅዱን መላእክት፤ የቅዱሳም ጻድቃን እና የቅዱሳን ሰማዕታት በዓላት አብረው ይከበራሉ፡፡ ለአብነትም የሥላሴ፤ የአማኑኤል፤ የዐርባዕቱ እንስሳ፤ የሩፋኤል፤ የኪዳነ ምሕረት፤ የመጥምቀ መለኮት ዮሐንስ (ፅንሰቱ)፤ የእስጢፋኖስ፤ የወንጌላውያኑ ማቴዎስና የማርቆስ፤ የዘብዴዎስ ልጆች የያዕቆብና የዮሐንስ፤ የቶማስ ዘህንደኬ፤ የሐና፤ የአቡነ አረጋዊ፤ የቂርቆስ፤ የአባ ኤዎስጣቴዎስ፤ የአብርሃም፣ የይስሐቅና የያዕቆብ፤ የአብርሃ አጽብሐ ነገሥትና የሌሎችም ቅዱሳን በዓላት ተጠቃሾች ናቸው፡፡

በአጠቃላይ በዘመነ ጽጌ ዘወትር እሑድ፣ እሑድ በመላ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ማኅሌት በመቆም ታላቅ በዓል ይደረጋል፡፡ የዐርባ ቀኑ ዘመነ ጽጌ (ወርኀ ጽጌ) መታሰቢያነቱ ለቅድስት ድንግል ማርያምና ለጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ እመቤታችን ልጇን ይዛ ከሰሎሜና ከዮሴፍ ጋር ወደ ምድረ ግብጽ በተሰደዱ ጊዜ የደረሰባትን ጭንቅና ውኃ ጥም፤ ግፍና እንግልት ለማስታወስና ከግብጽ ወደ ሀገሯ ናዝሬት መመለስዋን (ሚጠቷን) ለመዘከር ሲባል በዘመነ ጽጌ የደመቀ አገልግሎት ይከናወናል፡፡ በዚህ ወቅት የሚቆመው የሰንበት ማኅሌቱ፣ መዝሙሩና ቅዳሴው እንደዚሁም የሚቀርበው የክብር ይእቲና የዕጣነ ሞገር ቅኔ ሁሉ በዘመነ ጽጌ ላይ የተመሠረተ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የጥቅምት ወር ፳፻፲ ዓ.ም ምልዓተ ጉባኤ መጠናቀቁን ተከትሎ ከቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

ጥቅምት ፳፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ስብሰባ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ንዑስ አንቀጽ 164 በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው ከጥቅምት 6 ቀን 2010 ዓ.ም. ጀምሮ የመንበረ ፓትርያርኩን አጠቃላይ ሰበካ መንሳዊ ጉባኤና ዓመታዊውን የቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ስብሰባ ለ15 ቀናት ሲያካሒድ ሰንብቷል፡፡

በዚሁ መሠረት ቅዱስ ሲኖዶስ የመክፈቻውን ሥርዓተ ጸሎት ካደረሰ በኋላ ወሳኝ በሆኑ የአጀንዳ ነጥቦች ተወያይቶ የሚከተሉትን ውሳኔዎች አሳልፎአል፡፡

  1. ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ በጉባኤው መክፈቻ ያደረጉት ታሪካዊ ንግግር የቤተ ክርስቲያናችንን ሁለንተናዊ ሕይወት የቃኘ፣ ለሀገራችንና ቤተ ክርስቲያናችን ዕድገትንና የሰላም አስፈላጊነትን በስፋት የገለፀ በመሆኑ ጉባኤው በሙሉ ድምፅ ተቀብሎታል፡፡
  2. የሠላሳ ስድስተኛውን የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንሳዊ ጉባኤ የገራ መግለጫ አንዳንድ ማሻሻያ በማድረግ የጋራ መግለጫው የ2010 በጀት ዓመት ተግባር ሆኖ ያገለግል ዘንድ ምልዓተ ጉባኤው ተስማምቷል፡፡
  3. የቤተ ክርስቲያናችን እምነትና ሥርዓተ አምልኮ እስከ አሁን ደረስ ተከብሮና ተጠብቆ እንደኖረ ሁሉ አሁንም ከመንበረ ፓትርያርክ እስከ አህጉረ ስብከት የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ያለው የመንፈሳዊና የማኅበራዊ አገልግሎት መዋቅር በበለጠ ተጠናክሮ ይቀጥል ዘንድ መመሪያ ተሰጥቷል፡፡
  4. በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ሒሳብና በጀት መምሪያ ተዘጋጅቶ የቀረበው የ2010 ዓ.ም. በጀት የክፍያው ጣሪያ ተጠብቆ ሥራ ላይ እንዲውል ምልዓተ ጉባኤው ተስማምቷል፡፡
  5. የአንድ ሀገር ዕድገትና መሠረታዊ ፍላጎት ግቡን ሊመታ የሚችለው የሃይማኖቱና የሞራል ስሜቱ የማይወቅሰውን በሚሠራ፣ በመልካም ስነ ምግባር በታነፀ፣ የሥራን ክቡርነት በተረዳና እግዚአብሔርን መፍራት የጥበብ መጀመሪያ መሆኑን ባስተዋለ ትውልድ ተደግፎ ሲገኝ ስለሆነ፣ ኅብረተሰቡ ይህኑ በመረዳት
  • በትዕግሥትና በመቻቻል፣
  • በመካባበርና በመናበብ፣
  • በመደማመጥና በመግባባት መንፈስ በአንድነት ተባብሮ እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን አስተላፏል፡፡
  1. የነገድ፣ የሃይማኖትና የጾታ ልዩነት ሳይኖር ለጋራ ህልውና ለጋራ ልማትና ለጋራ ብልጽግና ለሀገራችን ኢትዮጵያና ለጎረቤት አህጉር ብሩህ ተስፋ ሰንቆ እንደሚመጣ የተነገረለት የዓባይ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ፕሮጀክት ኢትዮጵያዊነቱን እያስመሰከረ ስለመጣ አሁንም የፕሮጀክቱ ሥራ አሁንም የፕሮጀክቱ ሥራ ተጠናክሮ ለውጤት እስከሚበቃ ድረስ ሁሎችም ኢትዮጵያውያን አስፈላጊውን ድጋፍ በመለገስ እንዲተባበሩ ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፡፡
  2. ትውልድ ሁሉ የሙያና የስነ አእምሮ ብቃቱን አሳድጎ ሥራ የመፍጠር ክሂሎቱን እንዲያረጋግጥ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን አስተላልፏል፡፡
  3. ዕቅድን በተግባር ለማረጋገጥ
  • ሠርቶ ለማግኘት
  • ውሎ ለመግባት
  • አድሮ ለመነሣት
  • ዘርቶ ለማምረት
  • ነግዶ ለማትረፍና በነፃነት ለመኖር ሰላም ያስልጋል፡፡

ስለዚህ ሀገራችን ኢትዮጵያ ለአፍሪካ አህጉር የነፃነት ምልክት እንደሆነች ሁሉ የሰላምና የጸጥታም ምልክት መሆን አለባት፤ ከዚህ አንፃር ሰሞኑን በተለያየ ምክንያት በወገኖቻችን መካከል የተከሰተው ግጭት ተወግዶ ሙሉ ሰላምን የማስፈኑ ሥርዓት ተፋጥኖ እንዲረጋገጥ፣ ከዚህም ጋር በግጭቱ ምክንያት ለተጎዱ ወገኖቻችን ከመንበረ ፓትርያርክ እስከ አህጉረ ስብከት የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ድረስ ባለው መዋቅር ብር 6,000,000 (ስድስት ሚሊዮን) የገንዘብ ድጋፍ እንዲደረግ፡፡ እንዲሁም ከጥቅምት 27 ቀን 2010 ዓ.ም. ጀምሮ በመላ አገሪቱ ባሉት ገዳማትና አድባራት ለሁለት ሱባዔ ማለትም ለ14 ቀናት ያህል ጸሎተ ምሕላ እንዲደረግ ተወስኗል፡፡

  1. በውጭ ሀገር ከሚኖሩት አባቶች ጋር ቀደም ሲል ተጀምሮ የነበረው ዕርቀ ሰላም አሁንም ተጠናክሮ እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ አሳልፎአል፡፡
  2. በቃለ ዓዋዲው የቤተ ክርስቲያናችን መተዳደሪያ ደንብ መሠረት የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች የሆኑት ወጣቶች በየአጥቢያ ቤተ ክርስቲያናቸው በሰንበት ትምህርት ቤት ተደራጅተው በየሰበካ ጉባኤው አመራር ሰጭነት እንዲማሩ ምልዓተ ጉባኤው አመራርን ሰጥቷል፡፡
  3. በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት የሚገኘው የዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም የካህናት ማሠልጠኛ ተቋም ወደ ኮሌጅ ደረጃ ማደግ ያስችለው ዘንድ ከክፉሉ ሊቀ ጳጳስ የቀረበውን ፕሮፖዛል ጉባኤው ተቀብሎ አጽድቆታል፡፡
  4. በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም መንፈሳዊ ማሠልጠኛ አቋቁመው ለሚንቀሳቀሱ የተለያዩ ማኅበራት የሚያገለግል እስካሁን ድረስ የተዘጋጀ የማኅበራት ማደራጃ ደንብ የሌለ በመሆኑ ለወደፊቱ ሕገ ቤተ ክርስቲያኑንና ቃለ ዓዋዲውን መሠረት ያደረገ የማኅበራት ማደራጃ ደንብ በሕግ ባለሙያዎች እንዲዘጋጅ ጉባኤው ተስማምቶ ወስኗል፡፡
  5. በጋሻው ደሳለኝ የተባለ ግለሰብ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ለበርካታ ዓመታት ለምእመናን ሲያስተላልፍ የነበረው የክህደት ትምህርት በመረጃ ተስብስቦ ችግሩ ለቅዱስ ሲኖዶስ ከቀረበ በኋላ ከ15/02/2010 ዓ.ም. የክህደት ትምህርቱን በማውገዝ ከቤተ ክርስቲያናችን እንዲለይ ተደርጓል፣ በቤተ ክርስቲያናችን ስም እንዳያስተምር ተወግዟል፡፡
  6. በተመሳሳይ መልኩም በአሜሪካን ሀገር በዋሽንግተን ዲ.ሲ. የሚያገለግሉት አባ መዓዛ ክርስቶስ በየነ እያስተማሩ ያለው የክህደት ትምህርት ለቅዱስ ሲኖዶስ በመረጃ ቀርቦ የተረጋገጠባቸው ስለሆነ ሥልጣነ ክህነታቸው ተይዟል፤ ያሉበትን ቤተ ክርስቲያን ጨምሮ በማናቸውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እንዳይሰጡ ታግደዋል፡፡
  7. ወልደ አብ በሚል ርእስ፤ ገብረ መድኅን በተባለ ግለሰብ የተጻፈው የክህደትና የኑፋቄ ትምህርት የቅብዓትንና የጸጋን የክህደት ትምህርት የሚያስፋፋ በመሆኑ ካህናትን ከካህናት ምእመናንን ከምእመናን የሚያጋጭ ከመሆኑ ጋር፤ ከቤተ ክርስቲያናችንም አልፎ በሀገራችን ሁከት ለማስነሣት ታስቦ የተዘጋጀ ሆኖ ስለተገኘ፣ መጽሐፉ ከማናቸውም አገልግሎት እንዲለይ ተወግዟል፡፡
  8. ለገዳማት መተዳደሪያ እንዲሆን የተዘጋጀው ደንብ ረቂቁ ተስተካክሎ የቀረበ በመሆኑ በሥራ ላይ እንዲውል ጉባኤው ተስማምቷል፡፡
  9. ተሐድሶ እየተባለ የሚጠራው የኑፋቄ እምነት ማኅበር እራሱን ኦርቶዶክሳዊ በማስመሰል የቤተ ክርስቲያኒቱን ህልውና እየተፈታተነ ከማስቸገሩ የተነሣ ቅዱስ ሲኖዶስ ቀደም ሲል ፀረ ተሐድሶ ኮሚቴ በየአህጉረ ስብከቱ ተቋቁሞ የመከላከልና ቤተ ክርስቲያኒቱን የመጠበቅ ሥራ እንዲያከናውን ውሳኔን መስጠቱ የሚታወስ ነው፡፡ አሁንም ከቤተ ክርስቲያኒቱ ማዕከላዊ አስተዳደር እስከ አህጉረ ስብከት ባለው መዋቅር የተቋቋመው ፀረ ተሐድሶ ኮሚቴ ተጠናክሮ የመከላከሉን ሥራ እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ አመራር ሰጥቷል፡፡

ምልዓተ ጉባኤው ከዚህ በላይ በተገለፁትና በሌሎችም መንፈሳዊና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ አስፈላጊውን መመሪያ ከሰጠ በኋላ ስበስባውን በጸሎት አጠናቆአል፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን ለሀገራችንና ለዓለሙ ሁሉ ሰላሙን፣

ለሕዝባችን ፍቅር አንድነቱን ይስጥልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ጥቅምት 21 ቀን 2010 ዓ.ም.

አዲስ አበባ – ኢትዮጵያ

በኬንታኪ የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር መካሔዱን የአሜሪካ ማእከል አስታወቀ

ጥቅምት ፲፱ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን አሜሪካ ማእከል በኢንዲያና ግንኙነት ጣቢያ አዘጋጅነት ጥቅምት ፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በኬንታኪ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የመጀመርያው የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር መካሔዱን የአሜሪካ ማእከል አስታወቀ፡፡

የመርሐ ግብሩ ዓላማ ምእመናኑ ቃለ እግዚአብሔርን እንዲማሩና በመንፈሳዊ ሕይወታቸው እንዲበረቱ፣ ለሃይማኖታዊ ጥያቄዎቻቸውም ከቤተ ክርስቲያን አባቶች ምላሽ እንዲያገኙ ለማገዝ መኾኑን የግንኙነት ጣቢያው ለአሜሪካ ማእከል የላከው መረጃ ያመላክታል፡፡

የኬንታኪ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በሰሜን አሜሪካ የመጀመሪያውና ብቸኛው የጠበል አገልግሎት የሚሰጥበት ቦታ መኾኑን የጠቀሰው ግንኙነት ጣቢያው ምእመናን ጠበል እንዲጠመቁና ከበረከቱ እንዲሳተፉ ለማድረግ፣ እንደዚሁም የአግልግሎት ትጋት ልምድን ከአጥቢያው ካህናትና ምእመናን ቀስመው አርአያነት ላለው አገልግሎት እንዲነሣሡ ለማበረታታት መርሐ ግብሩ በኬንታኪ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን እንዲካሔድ መደረጉን ገልጿል፡፡

የግንኙነት ጣቢያውን መረጃ ዋቢ በማድረግ የአሜሪካ ማእከል የላከልን ዘገባ እንደሚያመላክተው መነሻውን ከኢንዲያናፖሊስ ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ባደረገውና ከአንድ መቶ ሠላሳ አምስት የሚበልጡ ምእመናንን ባሳተፈው በዚህ የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በጉዞ ወቅት በአውቶቡሶች ውስጥ የውይይት እና የመዝሙር አገልግሎት ለሁለት ሰዓታት ያህል ተሰጥቷል፡፡

ምእመናኑ ከቦታው በደረሱ ጊዜም በደብሩ ማኅበረ ካህናትና ምእመናን አቀባበል የተደረገላቸው ሲኾን፣ መርሐ ግብሩ በጸሎተ ኪዳን ከተጀመረ በኋላ የኬንታኪ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ሊቀ ካህናት አያልነህ የእንኳን ደኅና መጣችሁ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡ በመልእክታቸውም ሕዝበ ክርስቲያኑ በቅዱስ ገብርኤል ጠበል በመጠመቅ እያገኘ ያለውን ፈውስ አስረድተው የመርሐ ግብሩ ተሳታፊዎችም ጠበል በመጠመቅና በመጠጣት ከቅዱስ ገብርኤል በረከት እንዲሳተፉ አሳስበዋል፡፡

የሊቀ ካህናት አያልነህን ማሳሰቢያ ተቀብለው ምእመናኑ ጠበል ከተጠመቁና ከጠጡ በኋላ የጠዋቱ መርሐ ግብር የተጀመረ ሲኾን፣ በመርሐ ግብሩም “የተሰወረ መዝገብ” በሚል ርእስ በቀሲስ ኅብረት የሺጥላ ሰፊ ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል፡፡

እንደዚሁም በሊቀ ማእምራን ዓባይ አጥሌ፣ በሊቀ መዘምራን ይልማ ኃይሉ እና በደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤት መዘምራን ልዩ ልዩ ዝማሬዎች ቀርበዋል፡፡

ከምሳ ሰዓት በኋላም መልአከ ሰላም ቀሲስ ዶ/ር መስፍን ተገኝ የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴን የሚመለከት ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ ከምእመናን ለተነሡ ልዩ ልዩ ጥያቄዎችም በቤተ ክርስቲያን መምህራን ምላሽ ተሰጥቷል፡፡

የኢንዲያና ግንኙነት ጣቢያ ለአሜሪካ ማእከል በላከው መረጃ እንደ ገለጸው መዝሙር በማቅረብ፣ ትምህርቶችን በመከታተልና በጥያቄና መልስ ውድድሮች በመሳተፍ ሕፃናት ጭምር በሐዊረ ሕይወቱ የታደሙ ሲኾን፣ በቀረቡት ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ዝግጅቶችም ምእመናኑ ተደስተዋል፡፡

እንደ ግንኙነት ጣቢያው ማብራሪያ ዲያቆን አሮን እና ዲያቆን ኖሃ የተባሉ ሕፃናት “በሕይወቴ በዘመኔ ደስ የሚለኝ ለኔ በወንጌል ማመኔ” የሚለውን መዝሙር በገና እየደረደሩ ባቀረቡበት ሰዓት የመርሐ ግብሩ ተሳታፊዎች በሕፃናቱ ችሎታ የተሰማቸውን ደስታ በዕልልታ ሲገልጹ ተስተውሏል፡፡

የኢንዲያና ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል እና የኬንታኪ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል አብያተ ክርስቲያናት ሰበካ ጉባኤያት እንደዚሁም ሰንበት ት/ቤቶቹ ከኢንዲያና ግንኙነት ጣቢያ ጋር በአንድነት መሥራታቸው ለሐዊረ ሕይወቱ በስኬት መከናወን የላቀ ሚና የነበረው ሲኾን፣ በመርሐ ግብሩ ማጠቃለያም የግንኙነት ጣቢያው ሰብሳቢ ዶክተር በላይነህ ደስታ ለሐዊረ ሕይወቱ በስኬት መከናወን ትልቅ አስተዋጽዖ ላበረከቱ አካላት ዅሉ በማኅበረ ቅዱሳን ስም መንፈሳዊ ምስጋና አቅርበዋል፡፡

በመጨረሻም ከምእመናኑ የተገኘው $1747 (አንድ ሺሕ ሰባት መቶ ዐርባ ሰባት ዶላር) መርሐ ግብሩ ለተካሔደበት ለኬንታኪ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ገቢ ከተደረገ በኋላ መርሐ ግብሩ በአባቶች ጸሎት ተፈጽሟል፡፡

ከመናፍቃን ስውር ደባ ራሳችንን እንጠብቅ

ጥቅምት ፲፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከዲያብሎስ ጋር ተጋድሎዋን የጀመረችው በዓለመ መላእክት ነው፡፡ ቀስቱን ወርውሮ ዝናሩን አራግፎ ቤተ ክርስቲያንን ማሸነፍ ያልቻለው ዲያብሎስ ዛሬም በብዙ መልኩ እየተዋጋት ይገኛል፡፡ በማዕበል መካከል በምትቀዝፍ መርከብ የምትመሰለው ቤተ ክርስቲያን ሁልጊዜም አሸናፊ መሆኗ የታመነ ነው፡፡ ችግሩ መርከቧ ማዕበሉን ብትሻገርም በማዕበሉ የሚናወፁ መኖራቸው ነው፡፡ ከመርከቧ ተሳፋሪዎች ውስጥ ጥቂቶቹ በዓላማ አንዳንዶቹ ደግሞ በየዋህነት በማዕበሉ ተናውጠው ወድቀዋል፡፡ በዓላማ የሚወጡት ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ በመልእክቱ “ከእኛ ዘንድ ወጡ፥ ዳሩ ግን ከእኛ ወገን አልነበሩም፤ ከእኛ ወገንስ ቢሆኑ ከእኛ ጋር ጸንተው በኖሩ ነበር፤ ነገር ግን ሁሉ ከእኛ ወገን እንዳልሆኑ ይገለጡ ዘንድ ወጡ” ብሎ የተናገረላቸው ናቸው (፩ኛ ዮሐ. ፪፥፲፱)፡፡

እነዚህ ለጥፋት የቆሙና ለገንዘብ ወይም ለሌላ ስውር ዓላማ ቤተ ክርስቲያንን የተዉ ናቸው፡፡ በየዋህነት የሚወጡት ግን በዕውቀት ማነስ፣ በይሉኝታና በመሳሰሉት ተታለው፣ በጠላት ወጥመድ ተጠልፈው የጠፉ ናቸው፡፡ እነዚህ ቀናውን መንገድ (በጎውን) የሚያሳያቸው ቢያገኙ የሚመለሱ ናቸው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ጠላቶች እነዚህን የዋሃን የሚያጠምዱባቸው ብዙ ዘዴዎች አሏቸው፡፡ ከእነዚህ መካከል የኅትመትና የምስል ወድምፅ ውጤቶችን በቅዱሳት ሥዕላት አስውበው በማውጣት የዋሃንን ማደናገርና ከቻሉ በቅዱሳት ሥዕላቱ ሸፍነው የሚፈልጉትን የኑፋቄ ትምህርት የቤተ ክርስቲያን አስመስሎ ማቅረብ ነው፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳት ሥዕላት ትልቅ ቦታ ይሰጣቸዋል፡፡ ቅዱሳት ሥዕላትን በሚገባቸው ቦታዎች ላይ ማስቀመጥና የሚገባቸውን ክብር መስጠት ኦርቶዶክሳዊ ትውፊት ነው፡፡ መንፈሳዊ መጻሕፍት ሲጻፉ በመጻሕፍቱ ውስጥ ታሪካቸው የተጠቀሱትን ቅዱሳን ሥዕል በፊት ገጽ ወይም በውስጥ ገጽ ማስቀመጥም የተለመደ ነው፡፡ ምእመናንም በጸሎት ቤታቸው ቅዱሳት ሥዕላትን በማስቀመጥ ለቅዱሳን የሚገባውን ክብር ይፈጽማሉ፡፡ ቅዱሳት ሥዕላትና ኦርቶዶክሳዊ ትውፊት ትልቅ ትስስር ያላቸው ናቸው፡፡ በዚህ ምክንያት ተሐድሶ መናፍቃን በቅዱሳት ሥዕላት የተሸፈኑ የኑፋቄ መጻሕፍትን ገበያ ላይ እስከሚያወጡ ድረስ የቅዱሳንን ሥዕል የያዘ መጽሐፍ ኦርቶዶክሳዊ መጽሐፍ እንደሆነ “ግምት ይወሰድ” ነበር፡፡ በጎውን ሁሉ የሚጠላና ለማስጠላት የሚሠራ ዲያብሎስ ዛሬ ላይ ቅዱሳንን ለማስጠላት ያነሣሣቸው አንዳንዶች የፊት ገጻቸው የቅዱሳን ሥዕላት ውስጣቸው ደግሞ ቅዱሳንን የሚሳደቡ መጻሕፍትን በማሳተም እያሠራጩ ነው፡፡

ከእነዚህ መጻሕፍት መካከል በ፳፻፬ ዓ.ም የተወገዘው፣ የከሣቴ ብርሃን ድርጅት አባል የሆነው ጌታቸው ምትኩ የጻፈው “ገድል ወይስ ገደል” የሚለው መጽሐፍ አንዱ ነው፡፡ ይህ መጽሐፍ በፊት ለፊት ገጹ የአቡነ አረጋዊን ሥዕል የያዘ ሲሆን ውስጡ ግን ቅዱሳንን የሚሳደብና የሚነቅፍ ነው፡፡ “አቡነ ተክለ ሃይማኖት እግራቸውን ያጡት በጸሎት ሳይሆን በጦርነት ነው” ከሚለው ውሸት ጀምሮ የቅዱሳንን ተጋድሎ በማናናቅ በጸጋው የሚገኘውን ድኅነት በራሳቸው ጥረት የተኩ አድርጎ የሚያቀርብ የኑፋቄ መጽሐፍ ነው፡፡

“መሪጌታ ሠረቀ ብርሃን ዘወንጌል” በሚል ስም የተጻፈው “የዘመናት እንቆቅልሽ ሲፈታ” የሚለው የኑፋቄ መጽሐፍም ሌላኛው ሁነኛ ማስረጃ ነው፡፡ መጽሐፉ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስን ሥዕል የሽፋን ገጹ ላይ በመለጠፍ የዋሃንን የሚያደናግር ነው፡፡ መጽሐፉን ወደ ውስጥ ገጹ ዘልቀን ስናየው ግን ቅዱሳንን አንድ በአንድ እያነሣ የሚሳደብ ነው፡፡ ብዙዎቹ የተሐድሶ መናፍቃን ጽሑፎች ሰይጣን “ጠላቶቼን ስደቡልኝ” ብሎ የቀጠራቸው ጸሓፊዎች የጻፏቸው የሚመስሉና ቅዱሳንን የሚሳደቡ ናቸው፡፡ ይህ መጽሐፍም ከእነዚህ መጻሕፍት አንዱ ነው፡፡

ሌላኛው መጽሐፍ ደግሞ “በውኑ በማርያም ማመን ይገባሃልን?” በሚል ርእስ “መጋቤ ጥበብ ሰሎሞን” በተባለ ሰው የተጻፈው ነው፡፡ ይህ ግለሰብ በ፳፻፬ ዓ.ም ከተወገዙት ፲፮ መናፍቃን መካከል አንዱ ነው፡፡ መጽሐፉ በፊት ገጹ ላይ የእመቤታችንን ምስለ ፍቁር ወልዳ ሥዕል አድርጎ በውስጥ ገጹ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን የሚሳደብ መጽሐፍ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያደገ ሰው ይቅርና ጠላት እንኳን በእመቤታችን ላይ ሊናገረው የማይገባውን ብዙ ጸያፍ ነገር አካቷል፡፡ መጽሐፉ፣ ክብር ይግባትና “ማርያም ወላዲተ አምላክ መባል የለባትም”፤ “ከዮሴፍ ጋር በወንድና በሴት ልማድ ኖራለች”፤ “ከጌታችን ውጪ ሌሎች ልጆች አሏት”፤ “ቤተ ክርስቲያን የምታመልከው እግዚአብሔርን ሳይሆን ማርያምን ነው”፤ ወዘተ. የሚሉ የጽርፈት አሳቦችን የያዘ የኑፋቄና የክህደት መጽሐፍ ነው፡፡

ይህ መጽሐፍ ለሁለተኛ ጊዜ ሲታተም አዲስ መጽሐፍ ለማስመሰልና ርእሱም ገበያ ስለከለከለ የተሻለ እንዲሸጥ በሚል እኩይ አሳብ “በእንተ ማርያም” በሚል ርእስ ወጥቷል፡፡ “በእንተ ማርያም” የሚለው ሐረግ የአብነት ተማሪዎች ቁራሽ ለመለመን በየቤቱ ሲዞሩ የሚጠቀሙበት ቋንቋ ነው፡፡ ማንኛውም ኦርቶዶክሳዊ ይህን ቃል ያውቀዋል፡፡ “በእንተ ማርያም” ተብሎ ተለምኖ ሳይሰጥ ዝም ብሎ የሚያልፍ ኢትዮጵያዊ ምእመን የለም፡፡ ይህን በማሰብ ይመስላል ተሐድሶ መናፍቃኑ የመጽሐፉን ርእስ ከ “በውኑ በማርያም ማመን ይገባሃልን?” ወደ “በእንተ ማርያም” በመቀየር እመቤታችንን የሚሳደብ መልእክት ያስተላለፉት፡፡

ጸሓፊዎቹ ሲጽፉ ራሳቸውን “ዲያቆን”፣ “ቄስ”፣ “መምህር”፣ “መጋቤ ጥበብ”፣ “መጋቤ ሐዲስ”፣ ወዘተ. በሚል መዓርግና ስያሜ ነው፡፡ መጻሕፍትን ብቻ ሳይሆን በዚሁ መልክ ባለቤት አልባ በራሪ ወረቀቶችን፣ ጋዜጦችን፣ መጽሔቶችን፣ የድረ ገጽ ጽሑፎችን፣ ሲዲዎችን፣ ቪሲዲዎችን፣ ወዘተ ያወጣሉ፡፡ ለምሳሌ ይህ በራሪ ወረቀት የእመቤታችንን ሥዕል የያዘ ነገር ግን ኢየሱስ ክርስቶስ (ሎቱ ስብሐት) “አማላጅ እንደሆነ ለማስረዳት” ተብሎ የተሠራጨ የመናፍቃን ትምህርት ነው፡፡

በ፳፻፬ ዓ.ም ከተወገዙት ግለሰቦች መካከል አንዱ የሆነው ጽጌ ስጦታው ከግብረ አበሩ ጋር በመሆን ባወጡት ሲዲም ላይ ግለሰቦቹ በአለባበሳቸው የቤተ ክርስቲያን መምህር መስለው ከመቅረባቸውም በላይ የሲዲው የሽፋን ገጽ የድንግል ማርያምና የአባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ሥዕላትን ይዟል፡፡ እነዚህ ሁሉ ወጥመዶች የተዘረጉት ኦርቶዶክሳውያንን ከበረታቸው ለማስኮብለል ነው፡፡ እነዚህ መጻሕፍትና የምስል ወድምፅ ውጤቶች የእኛ መስለውን በስሕተት ገዝተናቸው ይሆናል፡፡ መጻሕፍቱን አንብበን፣ ሲዲዎችን ዐይተን የተደናገርንም እንኖር ይሆናል፡፡

ማንኛውንም ጉዳይ በሩቅ ዐይተን ውሳኔ ላይ ሳንደርስ ቀርበን መመርመር፣ ከእኛ በላይ የሆነውን እውነተኞች አባቶችን በመጠየቅ ራሳችንን ከስሕተት መጠበቅ ይገባናል፡፡ “በሩቅ ያዩት አህያ ፈረስ ይመስላል” እንደሚባለው በሽፋናቸው፣ በውጫዊ ይዘታቸው የሚበሉ መስለው ውስጣቸው የመናፍቃንን የክሕደት መርዝ የያዙ መጻሕፍት ይኖራሉ፡፡ መጻሕፍቱ ወይም የምስል ወድምፅ ውጤቶች ቅዱሳት ሥዕላትን ስለያዙ፣ በግእዝ ቋንቋ ስለተጻፉ ብቻ የእኛ ናቸው ማለት አይደለም፡፡

ከመናፍቃን ስውር ደባ ራሳችንን ለመጠበቅ ምን እናድርግ?

ተሐድሶ መናፍቃን በየጊዜው መልካቸውን እየቀያየሩ ከሚያዘጋጁት የጥፋት ወጥመድ ራሳችንን ከመከላከል እና ሌሎችን ከመጠበቅ አኳያ ማድረግ ያለብንን ጥቂት የጥንቃቄ ነጥቦችን እንመልከት፡-

፩ኛ. ቤተ ክርስቲያንን እና የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ማወቅ

ቤተ ክርስቲያን በሰማይ ያሉ የቅዱሳን፣ በምድር ያሉ የክርስቲያኖች አንድነት ናት፡፡ ይህች አንድነት አሐቲ፣ ቅድስት፣ ሐዋርያዊትና ኵላዊት ናት፡፡ ክርስቶስ በደሙ የመሠረታት ስለሆነች የክርስቶስ አካል ናት፡፡ የክርስቶስ አካሉ የሆነች ቤተ ክርስቲያንን ለማረም መነሣት “እግዚአብሔርን ለማረም” እንደ መነሣት ነው፡፡ በአስተምህሮዋም ነቅ የሌለባትና ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የተቀበለችውን ትምህርት ከሐዋርያት ጀምሮ ለዓለም ስትመግብ የኖረችና የምትኖር ናት፡፡ ትምህርቷ እንክርዳድ ያልተቀላቀለበት፣ እንግዳ የሆነ ትምህርት ያልታከለበት ጥንታዊና ቀጥተኛ ነው፡፡ አስተምህሮዋ ከአምላኳ የተቀበለችው ንጹሕ ዘር ነው፡፡ የምታስተምረው እግዚአብሔር ለዓለም የገለጠውን እውነት እንጂ ራሷ የፈጠረችውን ታሪክ አይደለም፡፡ የቤተ ክርስቲያን ድርሻ ከእግዚአብሔር የተቀበለችውን ለዓለም መመስከርና ማስተላለፍ እንጂ የተጣመመ ኖሮ ማቅናት፣ የጎደለ ኖሮ መሙላት፣ ያነሰ ኖሮ መጨመር፣ አላስፈላጊ የሆነ ኖሮ መቀነስ አይደለም፡፡ ሃይማኖት ከእግዚአብሔር ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽሞ የተሰጠች መንገድ ናት፡፡ ይህን ለማስተካከል መሞከር ራስን በእግዚአብሔር ቦታ ማስቀመጥ ነው፡፡

ስለዚህ ሁልጊዜም ቤተ ክርስቲያንን እና አስተምህሮዋን ለማወቅ መትጋት ያስፈልጋል፡፡ ብዙ ማወቅ የሚቻለው በመማር ነው፡፡ ስንማር ቤተ ክርስቲያንን እና የቤተ ክርስቲያን የሆነውን ሁሉ ማወቅ እንችላለን፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ሊቃውንትና መጻሕፍት ማወቅ እንግዳ በሆነ አዳዲስ ትምህርት ከመወሰድ ያድናል፡፡ “ሕዝቤ ዕውቀት ከማጣቱ የተነሣ ጠፍቷል” (ሆሴ. ፬፥፮) እንደተባለ ዕውቀት ማጣት ብዙ ችግሮችን ያመጣል፡፡ በሌሎች ካለመወሰድ አልፎ ሌሎችን ማትረፍ የሚቻለው በዕውቀት ላይ የተመሠረተ ክርስትናን ገንዘብ በማድረግ ነው፡፡ ስለዚህ ሁልጊዜ መማር፣ በመንፈሳዊ ዕውቀትና በመንፈሳዊ ሕይወት ማደግ ያስፈልጋል፡፡ ይህን ስናደርግ የቤተ ክርስቲያንን ድምፅ ከሌሎቹ ለይተን ማወቅ እንችላለን፡፡ የራሳችንን ካወቅን ደግሞ የሌሎችን የማደናገሪያ ቃል አንሰማም፡፡

፪ኛ. የቤተ ክርስቲያንን ጉዳይ ያገባኛል ብሎ መቀበል

ቤተ ክርስቲያን ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ባለው መዋቅሯ  ውሳኔዎችንና መመሪያዎችን ታስተላልፋለች፡፡ ውሳኔዎች እንዲፈጸሙ መመሪያዎች እንዲተገበሩ ሁሉም የድርሻውን መወጣት አለበት፡፡ ትግበራውን ለማገዝ መጀመሪያ የቤተ ክርስቲያንን ጉዳይ ጉዳዬ ብሎ መቀበል ያስፈልጋል፡፡ የኑፋቄ ትምህርት የሚያስተምሩ ሰዎች የሚወገዙት በትምህርት ያልበሰልነውን እንዳያታልሉ ነው፡፡ የኑፋቄ መጻሕፍት መልስ የሚሰጥባቸው እኛን ከኑፋቄ ለመጠበቅና በመንፈሳዊ ዕውቀታችን ለማሳደግ ታስቦ ነው፡፡ ትምህርት የሚሰጠው፣ ጉባኤ የሚዘጋጀው፣ የቤተ ክርስቲያን የውስጥ አገልግሎት የሚፈጸመው እንድናውቅ ብቻ ሳይሆን እንድንጸድቅም ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ዓላማ ልጆቿን በትምህርትና በምሥጢራት እግዚአብሔርን ወደ መምሰል ማሳደግ ነውና፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎችን መቀበል፣ ማክበርና መፈጸም፤ ጥያቄዎች ሲኖሩንም ኦርቶዶክሳዊ በሆነ መንገድ ማቅረብ፤ ከዚህም ባሻገር ከግለሰቦች ይልቅ ለቤተ ክርስቲያን መታዘዝ ኦርቶዶክሳዊ ትውፊት መሆኑን መረዳት አለብን፡፡ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ግን የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች እንዳይፈጸሙ የሚከለክሉ፣ በቤተ ክርስቲያን ስም ግለሰባዊ ፍላጎታቸውን የሚያራምዱ፣ ቅዱስ ሲኖዶስን የማውገዝ ሥልጣን የሌለው አስመስለው የሚያቀርቡ ተሐድሶ መናፍቃንን ሤራ ባለመረዳት የቤተ ክርስቲያንን መልእክት የማያከብሩ የዋሃን አሉ፡፡ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ከተወገዙ የተሐድሶ መናፍቃን ድርጅቶችና ግለሰቦች ጉባኤ ላይ የሚገኙ፤ የእነርሱን የኅትመትና የምስል ወድምፅ ውጤቶች የሚያከፋፍሉ፣ የሚሸጡ፣ የሚገዙ፣ የሚያነቡና የሚያዳምጡም አሉ፡፡ እነዚህ ሁሉ ክፍተቶች የተፈጠሩት የቤተ ክርስቲያንን መልእክት ጉዳዬ ብሎ ባለመስማትና ባለመቀበል ምክንያት ነው፡፡ ስለዚህ የቤተ ክርስቲያንን መልእክት ሰምቶ በመቀበል እንዲህ ዓይነት የመረጃ ክፍተቶችን መሙላት ከሁላችን ይጠበቃል፡፡

፫ኛ . ስለማናውቀው ነገር መጠየቅ

ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮዋን የምታስፋፋባቸው ብዙ መንገዶች አሏት፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ረድኤተ እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ የጻፏቸው ቅዱሳት መጻሕፍት ተጠቃሽ የአስተምህሮ ማስፋፊያ መንገዶች ናቸው፡፡ የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍት የምንላቸው የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ የሚያስጠብቁ ናቸው፡፡ እነዚህ መጻሕፍት የቤተ ክርስቲያን መሆናቸውን ማወቅ የምንችለው ያለንን ዕውቀትና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን በመጠቀም ነው፡፡ ስለዚህ የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍትን ከሌሎች ለመለየት የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ማወቅ ግድ ይሆናል፡፡ ይህም በአንድ ጀንበር የሚሳካ ቀላል ተግባር ባይሆንም መፍትሔው ግን ከባድ አይደለም፡፡ መጻሕፍትን ለመግዛት፣ የምናነባቸውን ለመምረጥ፣ ስናነብ ያልገባንን ለመረዳት፣ ትክክል መስሎ ያልታየን ወይም ያደናገረን ነገር ሲኖር ለማጥራት የቤተ ክርስቲያንን ሊቃውንት እና ከእኛ የተሻለ መንፈሳዊ ብስለት ያላቸውን መምህራን መጠየቅ መልካም ይሆናል፡፡

“ሊሆን ይችላል” ወይም “ለእኔ ተስማምቶኛል” በሚል ሰበብ ሳይገባንና በግል ፍላጎታችን ላይ ተመሥርተን የምንቀበለው “ትምህርት” ሊኖረን አይገባም፡፡ ሁልጊዜም ቢሆን ጠያቂ መሆንና ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ዕድገት ምክር የሚሰጡን መሪዎችን መፈለግና ምክራቸውን መተግበር ተገቢ ነው፡፡ ከዚሁ ሁሉ ጋርም ለትምህርት የምንፈልጋቸውን የኅትመትም ሆነ የምስል ወድምፅ ውጤቶች ስንገዛ ጥንቃቄ ማድረግ አለብን፡፡ በራሳችን ገንዘብ የመናፍቃንን ትምህርት ገዝተን ወደቤታችን ማስገባት የለብንም፡፡ ከመግዛታችን በፊት የጸሓፊውን ማንነት፣ የመጽሐፉን ይዘት ማወቅ፤ ካላወቅነውም መጠየቅ አስፈላጊ ነው፡፡ በስሕተት ገዝተናቸው ያነበብናቸውና ጥያቄ የፈጠሩብንም ካሉ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን በመጠየቅ መልስ ማግኘት አለብን፡፡

፬ኛ. መጻሕፍቱ መልስ እንዲሰጥባቸው ለሚመለከተው አካል ማቅረብ

ተሐድሶ መናፍቃን ባዘጋጁት ወጥመድ እንዳንሰናከል ለራሳችን ጥንቃቄ ከማድረግ ጎን ለጎን ሌሎችን የማዳን ሥራም ከሁላችን ይጠበቃል፡፡ የቤተ ክርስቲያን የሆነውን ካልሆነው መለየት የማንኛውም ክርስቲያን ግዴታ ነው፡፡ ባለማወቅ የሚደናገሩትን ከመጠበቅ አንጻር ግን የኅትመትና የምስል ወድምፅ ውጤቶቹ የእኛ አለመሆናቸውን ማወቅ ብቻ በቂ አይሆንም፡፡ ለሚመለከተው አካል ለማቅረብ የኅትመትና የምስል ወድምፅ ውጤቶቹ በማስረጃነት ያስፈልጋሉ፡፡ የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ የሚንዱ፣ ቤተ ክርስቲያንን የሚሳደቡ፣ ቅዱሳንን የሚያቃልሉ የኅትመትና የምስል ወድምፅ ውጤቶች ስናገኝ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ጥቅም ብለን ባንገዛቸውም የዋሃንን እንዳያደናግሩ መልስ እንዲሰጥባቸው አስበን መግዛት ይኖርብን ይሆናል፡፡ በእኛ ዐቅም መልስ ልንሰጥባቸው የማንችል ከሆነም እንኳን በላዔ መጻሕፍት ሊቃውንት ሞልተውናል፡፡ በስሕተት ገዝተን ያስቀመጥናቸው የተሐድሶ መናፍቃን የኅትመትና የምስል ወድምፅ ውጤቶች ለሊቃውንቱ በማቅረብ መልስ እንዲሰጥባቸው ማድረግ ይገባል፡፡ ይህን ስናደርግ ራሳችንንም ሆነ ሌሎችን ማትርፍ እንችላለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ማስገንዘቢያ

ይህ ጽሑፍ፣ ከመስከረም ፲፮ – ፴ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በወጣው የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ዕትም፣ በ “ንቁ” ዓምድ ሥር፣ “የተሐድሶ ስውር ደባ” በሚል ርእስ በገጽ ፮፣ ፯ እና ፲፭ ለንባብ መብቃቱን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡

ከሁለት ሺሕ በላይ አዳዲስ አማንያን የሥላሴን ልጅነት አገኙ

ጥቅምት ፲፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት በዐርባ ምንጭ ዙሪያ ወረዳ ቤተ ክህነት በዝጊቲ ደብረ ሰላም አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ከሁለት ሺሕ በላይ አዳዲስ አማንያን ጥቅምት ፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም ተጠምቀው የሥላሴን ልጅነት አገኙ፡፡

‹‹ይህን ያህል አዳዲስ ምእመናንን ማግኘታችን ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታላቅ ድል ነው›› ያሉት የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ኅሩያን ገሪማ ጌታነህ የጥምቀት መርሐ ግብሩ ቤተ ክርስቲያናችን መሥራት የሚገባትን ያህል ብትሠራ ከዚህ የበለጠ ድል አድራጊ እንደምትኾን ያመላከተ እንደ ነበረና ሀገረ ስብከቱ በቀጣይ ለሚሠራው ሥራ ከፍተኛ መነሣሣትን እንደ ፈጠረ አስረድተዋል፡፡

ተጠማቂዎቹ በሃይማኖታቸው ጸንተው እንዲኖሩ፣ ሥጋ ወደሙ እንዲቀበሉና ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንዳይለዩ ለማትጋት ሰባክያነ ወንጌልን መመደብ እና የንስሐ አባት እንዲኖራቸው ማድረግ በቀጣይ ሊሠራ የሚገባው ተግባር መኾኑንም ጨምረው ገልጸዋል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ እንደ ተናገሩት እነዚህ አዳዲስ አማንያን ወንጌልን ተምረው የክርስትና ጥምቀትን እንዲጠመቁና የሥላሴ ልጅነትን እንዲያገኙ ልዩ ልዩ ድጋፍ ካደረጉ ምእመናን መካከል ወለተ ማርያም እና ባለቤታቸው ኃይለ ኢየሱስ ከፍተኛውን ድርሻ ይወስዳሉ፡፡

በ፳፻፱ ዓ.ም በሀገረ ስብከቱ በደራሼና ኮንሶ አካባቢዎች የሚኖሩ በርካታ አዳዲስ አማንያን የክርስትና ጥምቀትን መጠመቃቸውን ያስታወሱት ሊቀ ኅሩያን ገሪማ ጌታነህ አሁንም እናት ቤተ ክርስቲያንን ተቀበይን በማለት የሚጣሩ ነፍሳት ከጊዜ ወደ ጊዜ መብዛታቸውን ተከትሎ በሀገረ ስብከቱ በሚገኙ ዐሥራ ዘጠኝ ወረዳ ቤተ ክህነቶች የጥምቀት መርሐ ግብሩ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡

የጥምቀት መርሐ ግብሩን በስፋት ለማስቀጠልና ተጨማሪ ምእመናንን ወደ ቤተ ክርስቲያን ለማምጣት ይቻል ዘንድም በመላው ዓለም የሚገኙ ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን በተቻላቸው አቅም ዂሉ ድጋፍ እንዲያደርጉ ሊቀ ኅሩያን ገሪማ ጌታነህ መንፈሳዊ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

አዳዲስ አማንያኑ በአባቶች ካህናት የክርስትና ማዕተብ ሲታሠርላቸው

በጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት የዐርባ ምንጭ ዙሪያ ወረዳ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሰላም አበባው ጌታኹን እንደ ገለጹት በአካባቢው ከፊሉ ኅብረተሰብ ሕይወቱን በአሕዛብነት የሚመራ ቢኾንም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሀገረ ስብከቱ፣ በወረዳ ቤተ ክህነቶችና በማኅበረ ቅዱሳን የጋራ ጥረት ከፍተኛ ቊጥር ያላቸውን ወገኖች የቤተ ክርስቲያን አባላት ለማድረግ ተችሏል፡፡

በወረዳው የሚገኙ ኢ አማንያንን በማስጠመቅ የቤተ ክርስያናችን አባል ለማድረግ አንዱ መሰናክል በአማንያኑ ቋንቋ ወንጌልን ማስተማር የሚችሉ ሰባክያነ ወንጌል እጥረት መኾኑን የጠቆሙት መልአከ ሰላም አበባው ወረዳ ቤተ ክህነቱ ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር በጋራ በመኾን ከሃያ በላይ ጋሞኛ ቋንቋ መናገር የሚችሉ ሰባክያነ ወንልን ማሠልጠኑንና በዚህም ፍሬያማ ሥራ መሠራቱን ገልጸዋል፡፡

በቀጣይም በልዩ ልዩ ቋንቋዎች ማስተማር የሚችሉ ሰባክያነ ወንጌልን አሠልጥኖ በመመደብ በወረዳው የሚገኙ ያልተጠመቁ ወገኖች በየቋንቋቸው ተምረው የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባላት እንዲኾኑ የማድረጉ ተልእኮ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስገንዝበዋል፡፡

አዳዲስ አማንያኑ በከፊል

በዛሬው ዕለት ሀብተ ወልድና ስመ ክርስትና ያገኙ ከሁለት ሺሕ በላይ አዳዲስ አማንያን በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ ለማበረታታትም ጋሞኛ ቋንቋን መናገር የሚችሉ ወጣቶችን በመመደብ የክትትልና የማስተማር ሥራቸውን እንደሚቀጥሉ መልአከ ሰላም አበባው ጌታኹን አስረድተዋል፡፡

‹‹የጠፉትን በጎች ለመፈለግ ከታቀደ ቆይቷል፡፡ በአካባቢው የክረምቱ ወራት በመግባቱ መርሐ ግብሩ ለተወሰነ ጊዜ ቢጓተትም በእግዚአብሔር ተራዳኢነት፣ በበጎ አድራጊ ምእመናን ጥረት ዕቅዳችን በዛሬው ዕለት እውን ኾኖ በርካታ የጠፉ በጎችን ፈልገን ለማግኘት ችለናል›› ያሉት ደግሞ የዝጊቲ ደብረ ሰላም አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም አስተዳዳሪ መምህር ቀለመ ወርቅ በላይ ናቸው፡፡

መምህር ቀለመ ወርቅ አያይዘውም ‹‹እነዚህ ጠፍተው የተገኙ፣ ሀብተ ወልድና ስመ ክርስትና ያገኙ በጎች ተመልሰው በተኵላ እንዳይነጠቁ በአካባቢያቸው በርካታ የስብከት ኬላዎችን በማዘጋጀት ምእመናኑ አምልኮተ እግዚአብሔርን እንዲፈጽሙ፣ በእምነታቸው እንዲጸኑና አቅማቸውን አጎልብተው የራሳቸውን ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን እንዲገነቡ የማስቻል ሥራ ሊሠራ ይገባል›› ሲሉ አሳስበዋል፡፡

አዳዲስ አማንያኑ ምሥጢረ ጥምቀት ከተፈጸመላቸው በኋላ

ከተጠማቂዎቹ መካከል አንዱ የኾኑት በዝጊቲ ባቆሌ ቀበሌ ነዋሪና የሌላ እምነት ተከታይ የነበሩት አቶ ዘሪኹን ቱሎ ‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የክርስቶስ አምላክነት የሚሰበክባት፣ በጠበልና በእምነት ከሕመም መዳን የሚቻልባት እውነተኛ ሃይማኖት እንደኾነች በእኛ አካባቢ የሚኖሩ ሰዎች ይነግሩኝ ነበር፡፡ ይህ ነገር ምን ያህል እውነት ነው እያልኹ ከራሴ ጋር ስሟገት ዓመታት ቢያልፉም ባለቤቴ ‹ወደ እናት ቤተ ክርስቲያን ተመለሱ› የሚል መልእክት በራእይ በመስማቷ ማንም ወደ ጥምቀቱ ሳያመጣን አምነን ተጠምቀን በዛሬዋ ዕለት የሥላሴን ልጅነት አግኝተናል›› በማለት የቤተ ክርስቲያን አባል የኾኑበትን ምሥጢር አስረድተዋል፡፡

አቶ ዘሪኹን የቤተ ክርስቲያን አባል ከመኾናቸው በፊት በገጠማቸው የጤና እክል ከዐሥር ዓመታት በላይ ሲሰቃዩ ኖረው በዝጊቲ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጠበል ተጠምቀው ከያዛቸው ደዌ እንደ ተፈወሱ፤ ከዚያም የተዋሕዶ ሃይማኖት አባል እንዲኾኑ ከተገለጠላቸው ራእይ ባሻገር መሠረት በጻድቁ አማላጅነት በተደረገላቸው ድንቅ ሥራ በመማረካቸው ከባለቤታቸው ጋር በኢየሱስ ክርስቶስ አምነው፣ ንስሐ ገብተው የክርስትና ጥምቀትን ተጠምቀው የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባል ለመኾን መብቃታቸውን ተናግረዋል፡፡

ከዝጊቲ ባቆሌ ማላላ መንደር የተገኘችው ወጣት ስመኝሽ አዦ በበኩሏ ‹‹እኔ በዛሬው ዕለት ለመጠመቅ የመጣሁት ማንም ሰው ቀስቅሶኝ ወይም ሒጂ ብሎኝ አልነበረም፡፡ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ፣ አባል እንድኾንባት ስመኛት የኖርኋት ሃይማኖት በመኾኗና የዛሬውን የጥምቀት መርሐ ግብርም ዳግመኛ የማገኘው ስላልመሰለኝ ይህን መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ከመላ ቤተሰቦቼ ጋር ተጠምቀን የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባል ኾነናል›› በማለት ወደ ክርስትና የመጣችበትን መንገድ ተናግራለች፡፡

ወጣት ስመኝሽ አዦ አይይዛም ‹‹ወደፊትም በሃይማኖቴ ጸንቼ እኖራለሁ፤ ቃለ እግዚአብሔር በመማርም በአካባቢዬ የሚኖሩ መናፍቃንና አሕዛብ ለሚጠይቁኝ ጥያቄ ምላሽ የሚኾን ስንቅን እቋጥራለሁ፤ እንደዚሁም በዝጊቲ አካባቢ የሚኖሩ የኅብረተሰብ ክፍሎችን በየቋንቋቸው እየተዟዟርኹ በማስተማር ቀጥተኛውንና እውነተኛውን መንገድ አሳያቸዋለሁ›› በማለት መንፈሳዊ ዕቅዷን ገልጻለች፡፡

ከተጠማቂዎች መካከል ከፊሉ ሥጋ ወደሙ ከተቀበሉ በኋላ

በጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት በዝጊቲ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ጥቅምት ፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በተከናወነው የጥምቀት መርሐ ግብር የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ፣ የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊና የትምህርት ክፍሉ ሓላፊ፤ የየወረዳ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጆችና ሠራተኞች፤ በጎ አድራጊ ምእመናን፤ ከአዲስ አበባና ከዐርባ ምንጭ የመጡ መምህራንና ዘማርያን፤ የማኅበረ ቅዱሳን አባላትና የዐርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤ ተማሪዎች፤ የዝጊቲና የአካባቢው ቀሳውስት፣ ዲያቆናትና ምእመናን በልዩ ልዩ የአገልግሎት ዘርፍ ተሳትፎ አድርገዋል፡፡

መረጃውን ያደረሰን የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ሪፖርተር ካሣኹን ለምለሙ ነው፡፡

የ፳፻፲ ዓ.ም የጥቅምት ወር ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤን መጀመር አስመልክቶ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የሰጡት ሙሉ ቃለ ምዕዳን 

ጥቅምት ፲፫ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ

አሐዱ አምላክ አሜን

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ወኤጲስ ቆጶሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት

እግዚአብሔር አምላካችን በተለመደው ቸርነቱ ከየመንበረ ጵጵስናችን በሰላም አሰባስቦ በዚህ ዓቢይ ዓመታዊ ስብሰባ ተገኝተን ስለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አንድነት፣ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት በስሙ እንድንመካከር ለፈቀደልን ለእርሱ ፍጹም ምስጋና ከአምልኮት ጋር እናቀርባለን፡፡

እናንተም ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትና ኤጲስ ቆጶሳት እንኳን በደኅና መጣችሁ፤ እንኳንም ለዚህ ሐዋርያዊና ቀኖናዊ የቅዱስ ሲኖዶስ ዓመታዊ ጉባኤ በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ!!

‹‹ወዘንተ ባህቱ አእምር ከመ በደኃሪ መዋዕል ይመጽኣ ዓመታት እኩያት ወይከውኑ ሰብእ መፍቀርያነ ርእሶሙ፤ ነገር ግን በኋኞቹ ዓመታት ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱበት ክፉ ዘመን እንደሚመጣ ዕወቅ›› (፪ ጢሞ ፫፥፩)

ይህ መልእክት ቅዱስ ጳውሎስ ለሚወደው ደቀመዝሙሩ ለጢሞቴዎስ ያስተላለፈው ምክር አዘል መልእክት ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ እንደሚታወቀው ዓይነቱ፣ ስልቱና መጠኑ ይለያይ እንደሆነ ነው እንጂ ከሆነ ጊዜ ጀምሮ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከፈተና ተለይታ አታውቅም፤ ይሁን እንጂ ወደመጨረሻው ዘመን አካባቢ የሚሆነው መከራ ግን ከሁሉ የባሰ እንደሚሆን በቅዱሳት መጻሕፍት በተደጋጋሚ የተገለፀ ነው፡፡

ከዚህ አኳያ ቅዱስ ጳውሎስ ተማሪውን ጢሞቴዎስን ሊያስገነዝበው የፈለገው ነገር በመጨረሻ ዘመን የሚከሠተውን ፈተና ምእመናን አውቀው ጥንቃቄ ያደርጉ ዘንድ እንዲያስተምር ነው፡፡ ለወደፊት የሚሆውን ነገር አስቀድሞ የማሳወቅና ወዳጆቹን የማስጠበቅ ኩነት ከጥንት ጀምሮ የነበረ የእግዚአብሔር አሠራር ነው፡፡ በዚህም ቅዱስ ጳውሎስ ለተከታዩ ትውልድ ስለመጨረሻው ዘመን ሁናቴ የማሳወቅ ሥራን ሲሠራ እናስተውላለን፡፡

በተጠቀሰው ክፍለ ምንባብ ላይ የመጨረሻው ዘመን ገጽታ ምን እንደሚመስል በዝርዝር ተገልጾአል፤ ይዘቱን ጠቅለል አድርገን ስንመለከተው በመጨረሻው ዘመን አካባቢ ነገሩ ሁሉ የተመሰቃቀለ እንጂ አንዳች የሚያስደስት ነገር እንደሌለው ነው፤ በተለይም በጥቅሱ ላይ እንደሚታየው የመጨረሻው ዘመን “ሰዎች ከምንም በላይ ራሳቸውን የሚወዱበት ጊዜ” መሆኑ ተነግሮአል፤ ይህ ዓይነቱ አመለካከት ቃለ ቅዱስ ወንጌልን ሙሉ በሙሉ የሚጻረር ነው፡፡

ጌታችን ለተከታዮቹ ያስተማረው “የኔ ሊሆን የሚወድ ሁሉ ራሱን ይካድ” የሚል ነው፡፡ ይህም ማለት የኋለኛው ትውልድ ራስን የሚወድ ከሆነ፣ ጌታ የሚያዘው ደግሞ ራስን መውደድ ሳይሆን ራስን መካድ ከሆነ ነገሩ “ሆድና ጀርባ” ሆኖአል ማለት ነው፤ ከዚህ አንጻር የዘመናችን ክሥተት በዚህ ፈተና ላይ ያለ እንደሆነ በግልፅ ማየት ይቻላል፡፡

ዛሬ የመንፈስ እናታቸው ብቻ ሳትሆን የማንነታቸውና የታሪካቸው ጭምር ማኅደር ከሆነች እናት ኦርቶዶክሳዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እያፈተለኩና እየኮበለሉ የሚገኙት በርካታ ወገኖች ራስን ከመውደድ የተነሣ ካልሆነ በቀር ሌላ ትርጉም ሊሰጠው አይችልም፡፡ ክርስቶስ ሌላ አዲስ ክርስቲያን የፈጠረ ይመስል ክርስቲያን የሆነውን ሰው በተለያየ አባባል ወደሌላ የክርስቲያን ጎራ እንዲኮበልል መጣጣር አስኮብላዩም ኮብላዩም ራስን ከመውደድ የተነሣ የሚያደርጉት ነው እንጂ አንዳች የሚጨበጥ ክርስቲያናዊ ትርጉም የለውም፡፡

ራስን በመውደድ የሚታወቀው የዘመናችን ባህርየ ሰብእ በዚህ ብቻ ሳይወሰን በትምህርትም፣ በሐሳብም፣ በአስተያየትም፣ በሥራም፣ ወዘተ የሚገለጸው ራስን ከፍ ከፍ የማድረግና የኔ ከሁሉ ይበልጣል እያሉ ሌላውን የማንኳሰስ አባዜ የሃይማኖት መዓዛ ምግባርን እየበከለው ይገኛል፡፡ ከዚህም የተነሣ የእኔ አውቅልሃለሁ ባይነት ዝንባሌ ሥር እየሰደደ ትሕትናና ፈሪሀ እግዚአብሔር የራቀው ትውልድ እየተበራከተ ይገኛል፡፡

ዛሬ እንደትናንቱ አበው ባሉት እንመራ፣ እንታዘዝ፣ አበውን እናዳምጥ የሚል ትውልድ ሳይሆን ከእናንተ ይልቅ እኛ እናውቃለንና እኛ የምንላችሁን ተቀበሉ በማለት ወደ ላይ አንጋጦ የሚናገር፣ ራስ ወዳድ የሆነ፣ መታዘዝን የሚጠላ ከሃይማኖታዊነት ይልቅ አመክንዮዋዊነትን የሚያመልክ ትውልድ እየመጣ ነው፡፡ ይህ ራስ ወዳድ አስተሳሰብ የሚመነጨው ዘመኑ ያፈራው የሥነ ልቡና ፍልስፍና እንጂ፣ ራሱን በመንፈስ ደሀ አድርጎና ሌላው ከእሱ እንደሚሻል አድርጎ ከሚያስተምር፣ በመንፈሰ እግዚአብሔር ከተጻፈው ከቅዱስ መጽሐፍ የመነጨ አይደለም፡፡

ቤተ ክርስቲያን ደግሞ መመሪያዋ በመንፈሰ እግዚአብሔር የተጻፈ ቅዱስ መጽሐፍ እንጂ በሰዎች ውሱን ጥበብ የተቀነባበረ ሰው ሠራሽ ፍልስፍናና ዘመን አመጣሽ ስልት አይደለም፡፡ በመሆኑም ቤተ ክርስቲያን ስትጠብቀው የኖረች ለወደፊትም የምትጠብቀው በመንፈሰ እግዚአብሔር በታጀበ ጥበብና ስልት እንጂ ከፍልስፍና ብቻ የተገኘ የተውሶ ዕውቀት ሊሆን አይችልምና ሁሉም ሊያስብበት ይገባል፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትና ኤጲስ ቆጶሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን ለሁለት ሺሕ ዓመታት ያህል በአንድነትና በጥንካሬ ጠብቆ ያቆየ ጥበብ ኦርቶዶክሳዊና ሲኖዶሳዊ የሆነ የውሉደ ክህነት አመራር ጥበብ እንጂ የምዕራባውያንና የሉተራውያን ምክር ቤታዊና ዘመን አመጣሽ ፍልስፍና አይደለም፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን መርሕ እንደዚያ ቢሆን ኖሮ ዛሬ የምናያት አንዲት ሐዋርያዊትና ኃያል ቤተ ክርስቲያን ሳትሆን የተበታተነች የደከመችና መዓዛ ሐዋርያት የሌላትና የተለያት ቤተ ክርስቲያን ነበር የምናየው፡፡

ይሁን እንጂ አባቶቻችን ካህናት መሪዎች፣ ሕዝቡ ተመሪ ሆኖ በአንድ የእዝ ሰንሰለት እየተደማመጠ ካህኑ ተናገረ ማለት እግዚአብሔር ተናገረ ማለት ነው በሚል ቅንና ትሕትና የተመላ ታዛዥነት እንደዚሁም በውሉደ ክህነት አመራር ሰጪነት የቤተ ክርስቲያናችን አንድነት እስከዛሬ ድረስ ተጠብቆ ቆይቷል፡፡

አሁን ግን ይህ ቀርቶ በአባቶች ላይ ተደራቢ አመራር ሰጪ፣ በአባቶች ላይ የስድብ ናዳ አውራጅ ትውልድ መበራከቱን ካየንና ከሰማን ውለን አድረናል፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ከጎናችን ሳይሆኑ ከጎናችሁ አለን የሚሉ ወገኖችም ስለድርጊቱ አፍራሽነት በተመለከተ አንድ ቀንስንኳ የተቃውሞ ሐሳብ አለመሰንዘራቸው በስተጀርባው እነርሱራሳቸው ያሉበት እንደሆነ የሚያመላክት መስሎ አሳይቶባቸዋል፡፡

አሁን ዋናው ጥያቄ፣ ይህ ራስ ወዳድ አመለካከት ተቀብሎ የሚመጣውን ጥፋት ማስተናገድ ይሻላል? ወይስ ራስን መካድ የሚለውን የጌታ ትምህርት አሥርፆ ነገሮች ሁሉ በንሥሐ ወደነበሩበት መመለስ፣ ምርጫውን ለዚህ ዓቢይ ጉባኤ አቅርበነዋል፡፡

በሌላ በኩል ቤተ ክርስቲያናችን ያላትን መንፈሳዊና ማኅበራዊ ተልእኮ በሚገባ ለማከናወን ግልፅነትንና ታማኝነትን በማረጋገጥ መልካም አስተዳደርን ማስፈን ለነገ የማይባል የቤተ ክርስቲያናችን ዓቢይ አጀንዳ ሆኖ ይገኛል፡፡ ከዚህ አኳያ የቤተ ክርስቲያናችንን ዙሪያ መለስ ምጣኔ ሀብት በሚገባ ለመያዝና ለማሳደግ እንዲሁም የሰው ኃይላችንን በአግባቡ ለመጠቀም የዘመኑን አሠራር መከተል የግድ ያስፈልገናል፡፡

ሌላው በሀገራችን እየተመዘገበ ያለውን የልማትና የዕድገት ግንባታ በአስተማማኝ ለማስቀጠል የሕዝቡ አንድነትና ሰላም መረጋገጥ ወሳኝነት አለው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ከሆነ ጀምሮ የኢትዮጵያ ሕዝብ የሰላም እናት ሆና ሕዝቡን በማስተማር ያስመዘገበችው ጉልህ ታሪክ ዛሬም ተጠናክሮ ይቀጥል ዘንድ ሁላችንም የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ኃላፊነታችንን እንድንወጣ በዚህ አጋጣሚ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

በመጨረሻም

ይህ ቅዱስ ጉባኤ የቤተ ክርስቲያኒቱን አንኳርና ዓበይት ጉዳዮችን በጥልቀት በመመርመርና በማጥናት ለቤተ ክርስቲያናችን ሊጠቅሙ የሚችሉ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ጉባኤው እንዲቀጥል እያሳሰብን እነሆ ዓመታዊው የጥቅምቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ መከፈቱን በእግዚአብሔር ስም እናበስራለን፡፡

እግዚአብሔር ጉባኤያችንን ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ሀገራችንንም ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ፣

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፣

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣

ጥቅምት ፲፪ ቀን ፳፻ወ፲ ዓ.ም፤

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ፡፡

ተዝካሩን አውጥቶ ክርስቶስን የተከተለ ሐዋርያ

ሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ

በዲያቆን ዘክርስቶስ ጸጋዬ

ጥቅምት ፲፫ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

አንድ ሰው ከቅፍርናሆም ገበያ ወደ ገሊላ ባሕረ ወደብ በሚወስደው ዐቢይ መንገድ ዳር ቁጭ ብሎ ነጋዴዎችን ቀረጥ ያስከፍል ነበር፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚያ ሲያስተምር ቀረጥ ከሚሰብስብበት ቦታ ጠርቶ ‹‹ተከተለኝ›› አለው፡፡ እርሱም ሥራውን ርግፍ አድርጎ ትቶ ተከተለው፡፡ ለሐዋርያነት በተጠራ ጊዜ በቤቱ ድግስ አዘጋጅቶ ለጌታችን ግብዣ አቅርቦ፣ ለድሆች መጽውቶ፣ የቁም ተዝካሩን አውጥቶ ክርስቶስን ተከተለው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ (ማቴ. ፱፥፲-፲፫)፡፡

ማቴዎስ ማለት ‹የእግዚአብሔር ስጦታ፣ ኅሩይ እመጸብሓን (ከቀራጮች መካከል የተመረጠ)› ማለት ነው፡፡ አባቱ ዲቁ እናቱ ደግሞ ክሩትያስ ይባላሉ፡፡ አባቱ (ዲቁ) በሌላ ስም ‹እልፍዮስ› (Aliphaeus) እየተባለ ይጠራል፡፡ ቅዱስ ማቴዎስ ብሔረ ሙላዱ (የተወለደበት አገር) ናዝሬት፤ ነገዱም ከነገደ ይሳኮር ነው፡፡ የቀድሞ ስሙ ‹ሌዊ› ነበር (ማር. ፪፥፲፬)፡፡ በዕብራውያን ዘንድ በሁለት ስሞች መጠራት የተለመደ ሲኾን ሌዊ ከቀድሞ ጀምሮ ይጠራበት የነበረ፤ ማቴዎስ ደግሞ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ከተከተለ በኋላ የተጠራበት ስሙ እንደ ኾነ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ያስረዳሉ፡፡

የቅዱስ ማቴዎስ ለሐዋርያነት መጠራት

ቅዱስ ማቴዎስ በቅዱሳን ሐዋርያት የስም ዝርዝር ላይ በራሱ ወንጌል በስምንተኛ፤ በማርቆስና በሉቃስ ወንጌል ደግሞ በሰባተኛ ቍጥር ተጠቅሷል (ማቴ. ፲፥፫)፡፡ በቀድሞ ሥራው ቀራጭ (የሮማውያን ግብር ሰብሳቢ) ነበር፡፡ የቀራጭነት ሥራውን ይሠራ የነበረውም በገሊላው ገዥ በሄሮድስ አንቲጳስ ሥር የነበረ ሲኾን ቦታውም በገሊላ ባህር አጠገብ በምትገኘው ደማቋ ከተማ ቅፍርናሆም ነበር፡፡ ዛሬ ይኼ ቦታ በእሾኽ ታጥሮ የጥንቱን የገበያ ምልክት ይዞ ይገኛል፡፡ የእልፍዮስ ልጅ ሌዊ በዚህ የመቅረጫ ቦታ ተቀምጦ የዓሣ እና የሌላም ነገር ንግድን እየተቆጣጠረ የቀራጭነት ሥራውን ይሠራ ነበር፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሚቀርጥበት ቦታ ጠጋ ብሎ ‹‹ተከተለኝ›› አለው፡፡ ቅዱስ ማቴዎስ ሲጠራ ቤት፣ ንብረት የነበረው ታዋቂ ባለ ሥልጣን ነበር፡፡ ጌታችን ‹‹ተከተለኝ›› ሲለው ድሆችን በነጻ የሚያበላ፣ ድውያንን በነጻ የሚፈውስ አምላክ መኾኑን ተረድቶ ሥራውን ርግፍ አድርጎ ትቶ ተከተለው፡፡ የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዝሙር መኾኑን በቤቱ ለጌታችንና ለተከታዮቹ ግብዣ በማድረግ ግልጥ አደረገ (ሉቃ. ፭፥፳፱)፡፡ ለጌታችና ለተከታዮቹ ግብዣ ያቀረበበት ቤቱም በቅፍርናሆም የሚገኝ ሲኾን ዛሬ ላቲኖች ቤተ ክርስቲያን ሠርተውበታል፡፡

የሐዋርያው አገልግሎት

ተዝካሩን ያወጣው ሐዋርያ ከክርስቶስ ጋር በነበረበት ጊዜ ከዋለበት እያዋለ፣ ካደረበት እያደረ፣ እንዲሁም በትንሣኤና በዕርገቱ ጊዜ በበዓለ ኀምሳ ደግሞ ለደቀ መዛሙርት መንፈስ ቅዱስ በወረደላቸው ጊዜ አብሮ ነበር (ማቴ. ፲፥፩-፭፤ ሉቃ. ፲፰፥፴፩)፡፡ ከዚያም ሰባቱ ዲያቆናት እስከ ተመረጡበትና እስጢፋኖስም እስከ ተገደለበት ቀን ድረስ ከዚያም በኋላ ለተወሰነ ጊዜ በኢየሩሳሌም ከሐዋርያት ጋር አብሮ ነበር፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት ዓለምን በዕጣ ሲከፋፈሉም ለእርሱ በደረሰው ሀገረ ስብከት በምድረ ፍልስጥኤም ገብቶ ጌታ ከፅንስ ጀምሮ ያደረጋቸውን ተአምራት፣ ያስተማረውን ትምህርት፣ የሠራውን ትሩፋት ቢነግራቸው ብዙዎች ከሕገ ኦሪት ወደ ሕገ ወንጌል፣ ከገቢረ ኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ ተመለሰው፣ በክርስቶስ አምነው ተጠምቀዋል፡፡

 በካህናት አገር ወንጌልን መስበኩ

ቅዱስ ማቴዎስ በደመና ተጭኖ በጌታችን ትእዛዝ ወደ ሀገረ ካህናት እንደ ተወሰደ በገድለ ሐዋርያት እና በመጽሐፈ ስንክሳር ተመዝግቦ እናገኛለን፡፡ በዚያም ወደ ከተማው መግቢያ ደጅ በደረሰ ጊዜ አንደ ወጣት ብላቴና አገኘ፡፡ ወደ ከተማው ለመግባት እንዴት እንደሚችል ቢጠየቀው ወጣቱ ብላቴናም ‹‹እራስኽንና ጺምኽን ካልተላጨኽ፣ በእጅህም ዘንባባ ካልያዝኽ መግባት እትችልም›› ሲል መለሰለት፡፡ ይህም ነገር ለሐዋርያው ማቴዎስ አስጨንቆት ሲያዝን አስቀድሞ ያነጋገረው ያ ወጣት ብላቴና ዳግም በስሙ ጠራው፡፡ ሐዋርያውም ‹‹ወዴት ታውቀኛለህ?›› አለው፡፡ እርሱም ‹‹እኔ ጌታህ ኢየሱስ ነኝ፤ አሁንም እንደ ነገርኹኽ አድርግ፡፡ እኔም ካንተ ጋር አለሁ፡፡ ካንተም አልርቅም›› አለው፡፡

ከዚያን በኋላ ጌታችን እንዳዘዘው አድርጎ ወደ ካህናት አገር ገባ፡፡ በዚያም ከጣዖቱ ካህናት አለቃ ከአርሚስ ጋር ተገናኘ፡፡ ከእርሱም ጋር ስለ አማልክቶቻቸው ተነጋገረና ‹‹ራሳቸውን ማዳን የልቻሉ ሌላውን እንዴት ያድናሉ?›› ብሎ ድንቅ ተአምራትን በማድረግ ጣዖቶቻቸውን አቃጠላቸው፡፡ በዚያን ጊዜም ከአርሚስ ጋር ብዙዎች ሰዎች አመኑ፡፡ ቅዱስ ማቴዎስም አጠመቃቸው፡፡ ከሰማይ ምግብ አውርዶም መገባቸው፡፡

የአገሩም ንጉሥ የሐዋርያውን ድንቅ ስራ በሰማ ጊዜ እጅግ ተቆጥቶ ከአርሚስ ጋር ሐዋርያውን ወደ እሳት በጨመረው ጊዜ ጌታችን ከእሳቱ አዳናቸው፡፡ ከዚያን በኋላ በሚያሰቃያቸው ነገር ሲያስብ ንጉሡ ልጁ መሞቱን ሰማ፡፡ በዚህም እያዘነ ሳለ ሐዋርያው ማቴዎስ ‹‹ልጅህን እንዲያስነሡት ወደ አማልክትህ ለምን አትለምንም?›› አለው፡፡ ንጉሡም ‹‹አማልክት የሞተ ማንሣት እንዴት ይችላሉ?›› ብሎ መለሰ፡፡ ቅዱስ ማቴዎስም ‹‹ብታምንስ የእኛ አምላክ ልጅኽን ከሞት ማስነሣት ይችላል›› አለው፡፡ ንጉሡም ‹‹ልጄ ከሞት ከተነሣ እኔ አምናሁ›› አለው፡፡ በዚያን ጊዜ ሐዋርያው ክብር ይግባውና ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸለየና የንጉሡንም ልጅ ከሞት አስነሣው፡፡ ንጉሡም በጌታችን አመነ፡፡ የአገሩ ሰዎችም ዂሉ አመኑ፡፡ የቀናች ሃይማኖትንም አስተምሮ ክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው፡፡ የጣዖቱ ካህን የነበረው አርሚስንም ኤጲስቆጶስ አድርጎ ሾመላቸው፡፡

የማቴዎስ ወንጌል

ጎርጎርዮስ ዘእንዚናንዙ የቅዱሳት መጻሕፍትን ቀኖና በጠቀሰበት ጽሑፉ ቅዱስ ማቴዎስ ከአይሁድ ወደ ክርስትና ለተመለሱ ዕብራውያን ወንጌሉን እንደ ጻፈው ሲገልጽ ‹‹ማቴዎስ ለዕብራውያን ተአምራተ ኢየሱስን ጻፈ›› በማለት ተናግሯል፡፡ በመቅድመ ወንጌል ትርጓሜ ላይም እንዲህ ይላል፤ ‹‹ምድረ ፍልስጥኤም ለማቴዎስ በዕጣ ደረሰችው፡፡ ከዚያ ገብቶ ጌታ ከፅንስ ጀምሮ ያደረገውን ተአምር፣ ያስተማረውን ትምህርት፣ የሠራውን ትሩፋት ቢነግራቸው እስራኤል ናቸውና ከኦሪት ወደ ወንጌል፣ ከገቢረ ኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ ተመለሱ፤ አመኑ፤ ተጠመቁ፡፡ ትምህርት ካልደሰበት ለማዳረስ ወጥቶ በሚሔድበት ጊዜም ‹በቃል ያለ ይረሳል፤ በመጽሐፍ ያለ ይወረሳል› ብለውት ጽፎላቸዋል››፡፡

የሐዋርያው አገልግሎት በኢትዮጵያ 

አውሳብዮስ ዘቂሣርያ እና ሩፊኖስ የጻፏቸው ማስረጃዎች እንደሚያስረዱት ቅዱስ ማቴዎስ በእስራኤል፣ በኢትዮጵያ፣ በፋርስ፣ በባቢሎን፣ በዓረቢያ፣ በግሪክ፣ በፍልስጥኤም እና በብሔረ ብፁዓን ወንጌልን አስተምሯል፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት ቅዱስ ማቴዎስ በአገራችን ኢትዮጵያ በትግራይ አካባቢ ከዓድዋ አውራጃ በስተምዕራብ ልዩ ስሙ ናዕይር በተባለው ቦታ ወንጌልን አስተምሯል፡፡

ሐዋርያው በብሔረ ብፁዓን

ሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ ብሔረ ብፁዓን በደመና ተጭኖ ሔዶ ማስተማሩን ገድለ ዞሲማስ (ዘሲማስ) ያስረዳል፡፡ ከቅዱስ ማቴዎስ በኋላ በብሔረ ብፁዓን ስለሚኖሩ ወገኖች አኗኗር በጥልቀት በቀሲስ ዞሲማስ የተዘረዘረ ሲኾን ለእነዚህ ወገኖች ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ቅዱስ ማቴዎስም ወንጌልን እንዳስተማሯቸው በመጽሐፈ ገድሉ ተጠቅሷል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዂልጊዜ በየበዓላቸው ወደ ብሔረ ብፁዓን መሔዱ፣ ቅዱስ ማቴዎስም ከቅዱሳን መላእክት እና ሄሮድስ ካስገደላቸው አንድ መቶ ዐርባ አራት ሺሕ ሕፃናት ጋር እግዚአብሔርን ማመስገኑ ተገልጿል፡፡

የሐዋርያው ተጋድሎና የምስክርነቱ ፍጻሜ

የቅዱስ ማቴዎስ ተጋድሎውና የምስክርነቱ ፍጻሜ ሲቃረብ ወደ አንዲት ከተማ ገብቶ አስተማረ፡፡ በዚያም ብዙዎችንም አሳመነ፡፡ አገረ ገዢውም ይዞ ከወኅኒ ቤት ጨመረው፡፡ በወኅኒ ቤቱም አንድ እጅግ የሚያዝን እስረኛ አገኘና ስለ ሐዘኑ ጠየቀው፡፡ እርሱም ብዙ የጌታው ገንዘብ ከባሕር እንደ ሰጠመበት ነገረው፡፡ ሐዋርያው ማቴዎስም እስረኛው የጠፋበትን ገንዘብ የሚያገኝበትን የባሕር ዳርቻ ጠቆመው፡፡ እስረኛውም ሐዋርያው በነገረው መሠረት የጠፋውን ገንዘብ አግኝቶ ለጌታውም ሰጠው፡፡ ጌታውም ከየት እንዳገኘው ቢጠይቀው ከወኅኒ ቤት ባገኘው በሐዋርያው ማቴዎስ ጥቆማ የጠፋውን ገንዘብ ሊያገኘው መቻሉን ነገረው፡፡ ጌታው ግን ሊያምነው አልቻለም ነበር፡፡

ይልቁንም እጅግ ተቆጥቶ ሐዋርያውን ከእስር ቤት አስወጥቶ ወደ ንጉሡ ወሰደው፡፡ ንጉሡም ተዝካሩን አውጥቶ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የተከተለውን ሐዋርያ ቅዱስ ማቴዎስን ወዲያው በሰይፍ ራሱን እንዲቆርጡት፣ ሥጋውንም ለሰማይ ወፎች እንዲጥሉት አዘዘ፡፡ የንጉሡ ወታደሮችም በታዘዙት መሠረት ጥቅምት ፲፪ ቀን በ፷ ዓ.ም የሐዋርያውን አንገት በሰይፍ ቆርጠው ራሱን ለብቻ፣ ሰውነቱን ለብቻ አድርገው አሞሮች እንዲበሉት ጥለውት ሔዱ፡፡ ምእመናንም ራሱንና ቀሪው ሰውነቱን በአንድ አድርገው ካባቶቹ መቃብር እንዲቀበር አደረጉ፡፡ ያ ሐዘንተኛ እስረኛም የቅዱስ ማቴዎስን መገደል ሲሰማ ለሦስት ቀናት እያዘነ አለቀሰ፡፡ ከቅዱስ ማቴዎስ ሞት በኋላ አምስት ቀናት ቆይቶ እርሱም ዐረፈ፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይኹን! እኛንም ተዝካሩን አውጥቶ፣ ሥልጣኑንና ሥራውን ትቶ፣ የሚበልጠውን ሰማያዊ መንግሥት ሽቶ ክርስቶስን በተከተለው ሐዋርያ በቅዱስ ማቴዎስ ጸሎት ይማረን፡፡ በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር፤ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡- የጥቅምት ፲፪ ቀን ስንክሳር እና ገድለ ሐዋርያት፡፡

ቅዱስ ማቴዎስ ወንጌላዊ

ቅዱስ ማቴዎስ ወንጌላዊ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ጥቅምት ፲፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም 

የጌታችን፣ አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አምላካዊ ትእዛዝ ተቀብለው ወንጌልን ለመላው ዓለም በማብሠር መምለክያነ ጣዖትን ወደ አሚነ እግዚአብሔር፣ አሕዛብን ወደ ክርስትና ከመለሱ ቅዱሳን ሐዋርያት መካከል ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ አንደኛው ነው፡፡ ቅዱስ ማቴዎስ አገሩ ናዝሬት፣ የዘር ሐረጉም ከይሳኮር ነገድ ሲኾን አባቱ እልፍዮስ (ዲቁ)፣ እናቱ ደግሞ ካሩትያስ ይባላሉ፡፡ ለደቀ መዝሙርነት ከመመረጡ በፊት ‹ሌዊ› ይባል ነበረ፤ ከተጠራ በኋላ ግን ‹ማቴዎስ› ተብሏል፡፡ ‹ማቴዎስ› ማለት በዕብራይስጥ ቋንቋ ‹ጸጋ እግዚአብሔር (የእግዚአብሔር ስጦታ)› ማለት ሲኾን ስሙን ያወጣለትም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ለወንጌል አገልግሎት የተጠራውም በቅፍርናሆም ከተማ ከቀራጭነት ሥራ ላይ ነው (ማቴ. ፱፥፱-፲፫፤ ሉቃ. ፭፥፳፯-፴፪)፡፡

ቅዱስ ማቴዎስ ቍጥሩ ከ፲፪ቱ ሐዋርያት ሲኾን ከ፬ቱ ወንጌሎች አንደኛውን የጻፈው እርሱ በመኾኑ ‹ወንጌላዊ› እየተባለ ይጠራል፡፡ ወንጌሉን የጻፈውም ጌታችን ባረገ በ፰ኛው ዓመት መጨረሻ በ፵፩ (፵፪) ዓ.ም፣ ቀላውዴዎስ ቄሣር በነገሠ በመጀመሪያው ዘመን ነው፡፡ ወንሉን የጻፈበት ቋንቋ ዕብራይስጥ ሲኾን ጽሕፈቱንም በፍልስጥኤም አገር ጀምሮ በህንድ ፈጽሞታል (ማቴ. ፳፰፥፳)፡፡

ቅዱስ ማቴዎስ ወንጌሉን የጻፈበት ምክንያትም በሀገረ ስብከቱ በፍልስጥኤም ጌታችን ከፅንስ ጀምሮ እስከ ዕርገቱ ድረስ ያደረጋቸውን ተአምራት፣ ያስተማረውን ትምህርትና የሠራቸውን ትሩፋቶች ሲያስተምራቸው ብዙ አሕዛብ ከኦሪት ወደ ወንጌል፤ ከገቢረ ኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ ተመልሰዋል፡፡ እነዚህ ምእመናን ‹‹በቃል ያለ ይረሳል፤ በመጽሐፍ ያለ ይወረሳልና ያስተማርኸንን ጻፍልን›› ብለውት፤ አንድም እንደ አባትነቱ ከራሱ አንቅቶ (አመንጭቶ)፤ አንድም አይሁድ ክርስቲያኖችን ‹‹ክርስቶስ ወልደ ዳዊት ወልደ አብርሃም መኾኑን ሠፍራችሁ፣ ቈጥራችሁ አስረዱን›› ቢሏቸው ለማስረዳት የዕውቀት ማነስ ነበረባቸውና እርሱ ጽፎላቸዋል፡፡

መምህራነ ቤተ ክርስቲያን እንደሚስተምሩት የማቴዎስ ወንጌል በውስጡ ከ፻፶ በላይ የብሉይ ኪዳን ጥቅሶችን ማካተቱ አይሁድን ለማሳመን የተጻፈ ለመኾኑ ማስረጃ ነው፡፡ የማቴዎስ ወንጌል ከኦሪታዊ ይዘቱ አኳያ በመጀመሪያ ተቀመጠ እንጂ የተጻፈው ግን ከማርቆስ ወንጌል ቀጥሎ እንደኾነም መምህራኑ ያስረዳሉ፡፡ ወንጌሉን ከጻፈ በኋላም ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሶ አፓንጌ በሚባል አገር ወንጌልን በመስበክ ብዙዎችን በክርስቶስ አሳምኗል፡፡ የማቴዎስን ወንጌል ወንጌላዊው (ሐዋርያው) ዮሐንስ በእልአንሳን፣ በህንድና በኢየሩሳሌም አገሮች እየተረጐመ አስተምሮታል፡፡ የእርሱ ስብከት በመጽሐፍ ቅዱስ አለመጠቀሱም መላ ሕይወቱን ለክርስቶስ አገልግሎት የሰጠ ሐዋርያ መኾኑን እንደሚያሳይ መምህራን ይመሰክራሉ፡፡

ቅዱስ ማቴዎስ በወንጌሉ ‹‹ወልደ ዳዊት፣ ወልደ አብርሃም›› በማለት የክርስቶስን ምድራዊ ልደት (ሰው መኾን) ጽፏልና ከአራቱ የኪሩቤል ገጽ መካከል በአንደኛው በገጸ ሰብእ ይመሰላል፡፡ የኤፌሶን ወንዝ ፈለገ ሐሊብ ይባላል፤ ርስትነቱም ለሕፃናት ነው፡፡ ቅዱስ ማቴዎስም በዘር የሚወለዱ አበውን ልደት ጽፏልና፤ ዳግመኛም ሄሮድስ ስላስፈጃቸው ሕፃናት ተናግሯልና በኤፌሶን ወንዝ ይመሰላል፡፡

ወንጌልን አስተምሮ ብዙዎችን ወደ አሚነ እግዚአብሔር ከመለሰ በኋላ ጌታችን ወደ ካህናት አገር እንዲሔድና የካህን ልብስ ለብሶ፣ ፀጉሩንና ጺሙን ተላጭቶ፣ በቀኝ እጁ ዘንባባ ይዞ ወደ አገሩ ቅፅር እንዲገባ ስላዘዘው በደመና ተጭኖ ሔዶ ወደ ቤተ ጣዖታቱ ገብቶ በጸለየ ጊዜ መብረቅ የመሰለ ብርሃን ወረደ፡፡ የአምላክን ከሃሊነት ለመግለጥ በተከሠተው ርዕደ መሬትም የአገሩ ጣዖታት ዂሉ ወድቀው ተሰባበሩ፡፡ አርሚስ የሚባለው የጣዖቱ ካህንም ካየው አምላካዊ ብርሃንና ድንቅ ተአምር የተነሣ በክርስቶስ አምኖ ከተጠመቀ በኋላ የቅዱስ ማቴዎስ ረድእ ኾኗል፡፡

ይህ ክሥተትም በአጭር ጊዜ ውስጥ ብዙዎችን በክርስቶስ እንዲያምኑ አድርጓቸዋል፡፡ ያማኞች ቍጥርም ፬ ሺሕ እንደ ነበረ በገድለ ሐዋርያት ተጠቅሷል፡፡ ከዚህ በኋላ የንጉሡ ልጅ በሞተ ጊዜ ቅዱስ ማቴዎስ ወደ እግዚአብሔር ጸልዮ ከሞት ቢያስነሣው ንጉሡ፣ ቤተሰቦቹና የአገሩ ሰዎች በኢየሱስ ክርስቶስ አምነው አጵሎን የተባለውን ጣዖት በእሳት አቃጥለው ቤተ ጣዖቱን የአምልኮተ እግዚአብሔር መፈጸሚያ ሥፍራ አድርገውታል፡፡ ቅዱስ ማቴዎስም አርሚስን ኤጲስ ቆጶስ በማድረግ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾሞላቸዋል፡፡

በገድለ ሐዋርያት እንደ ተጠቀሰው ቅዱስ ማቴዎስ ከማረፉ በፊት በደመና ተነጥቆ ብሔረ ብፁዓን ገብቷል፤ በዚያም ሄሮድስ በግፍ በጨፈጨፋቸው ሕፃናት ክብረ በዓል ጌታችን ወደ እነርሱ ሲመጣ፣ መላእክትም በዙሪያው ከበው ሲያመሰግኑት ያይ ነበር፡፡ ከዚያ ተመልሶም በየአገሩ እየዞረ ወንጌልን አስተምሯል፤ ካስተማረባቸው አገሮችም ፍልስጥኤም፣ ፋርስ፣ ባቢሎን፣ ኢትዮጵያና ዓረቢያ ይጠቀሳሉ፡፡ የማስተማር ተልእኮው የተከናወነውም በታንሿ እስያ ውስጥ ነው፡፡ ግሪካውያን አሕዛብ ‹‹አምላካችንን ሰደበብን›› ብለው አሥረውት በነበረ ጊዜም ወኅኒ ቤት ኾኖ ወንጌልን ይሰብክ ነበር፡፡

ቅዱስ ማቴዎስ በ፵ ዓ.ም በአገራችን በኢትዮጵያ እየተዘዋወረ ወንጌልን እንደ ሰበከና በዘመኑ የነበሩ ኦሪታውያን ነገሥታትን ጨምሮ በርካታ አሕዛብን አስተምሮ በማጥመቅ ወደ ክርስትና ሃይማኖት እንደ መለሰ፤ እንደዚሁም ለምጻሞችን በማንጻት፣ አንካሶችን በማርታት፣ ሕሙማንን በመፈወስ፣ ሙታንን በማስነሣት ድንቅ ድንቅ ተአምራትን እንዳደረገ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንትና በትግራይ ክልል በማኅበረ ጻድቃን ዴጌ ገዳም የሚገኙ የብራና መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡

ወንጌላዊው በአገልግሎቱ መጨረሻም በትርያ በምትባል አገር ሲያስተምር አገረ ገዥው አሠረው፡፡ በወኅኒ ቤቱም ጌታው ለንግድ የሰጠውን ገንዘብ ማዕበል ወስዶበት በዕዳ ምክንያት የሚያለቅስ አንድ እሥረኛ አገኘና አጽናንቶ መኰንኑ ገንዘቡን ከሕዝቡ ለምኖ እንዲከፍለው በመሻት ከእሥር እንደሚፈታው፤ ከባሕር ዳርቻም የወደቀ ወርቅ የተሞላ ከረጢት እንደሚያገኝ፤ ያንንም ለጌታው ከሰጠ በኋላ ከዕዳና ከእሥር ነጻ እንደሚኾን አስረዳው፡፡ ሰውየውም ቅዱስ ማቴዎስ የተናገረው ዂሉ ስለ ተፈጸመለት ‹‹በኢየሱስ ክርስቶስ አምናለሁ›› እያለ፤ ለቅዱስ ማቴዎስ እየሰገደ በኢየሱስ ክርስቶስ ማመኑን ተናገረ፤ ደስታውን ገለጸ፡፡

ይህንን ድንቅ ተአምር የሰሙ ብዙ አሕዛብም በጌታችን አምነዋል፡፡ በዚህ ምክንያት አርያኖስ በሚባል ንጉሥ ትእዛዝ ጥቅምት ፲፪ ቀን አንገቱን በሰይፍ ተቈርጦ በሰማዕትነት ዐርፏል፤ ምእመናንም ሥጋውን በክብር ቀብረውታል፡፡ ትርጓሜ ወንጌል ደግሞ ብስባራ በምትባል አገር በደንጊያ ተወግሮ በሰማዕትነት ካረፈ በኋላ የቂሣርያ ክፍለ ዕጣ በምትኾን በቅርጣግና መቀበሩን ይናገራል፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይኹን፡፡ እኛንም በሐዋርያው በቅዱስ ማቴዎስ ጸሎት ይማረን፤ በረከቱም ይደርብን፡፡

ምንጮች፡

  • መጽሐፈ ስንክሳር፣ ጥቅምት ፲፪ ቀን፤
  • የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት፤
  • የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፤
  • የማቴዎስ ወንጌል አንድምታ ትርጓሜ፤
  • ገድለ ሐዋርያት፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ወቅታዊ የአዘክሮ መልእክት

ጥቅምት ፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

‹‹ወንድሜ ሆይ፥ በጎ አድራጊ እንጂ ክፉ አድራጊ አትኹን፤›› (፫ኛ ዮሐ. ቍ. ፲፩)::

በጌታችን ላይ በአይሁድ የተፈጸመውን ዂሉ ለድኅነተ ሰብእ እንደ ተፈጸመ ተቀብለን ሐተታ ላለማብዛት ብንተወው እንኳን መልካም የሚሠሩትን ክፉ ስም እየሰጡ ቤተ ክርስቲያንን የሚከፋፍል ሥራ መሥራት የተጀመረው በዚያው በሐዋርያት ዘመን እንደ ኾነ ቅዱስ መጽሐፍ ይመሰክራል፡፡ ‹‹ከእነርሱ አንዳንዶች በቅናታቸውና በክርክራቸው፥ ሌሎችም በበጎ ፈቃድ ስለ ክርስቶስ ሊሰብኩና ሊያስተምሩ የወደዱ አሉ፡፡ በፍቅር የሚያስተምሩም አሉ፤ ወንጌልን ለማስተማር እንደ ተሾምኹ ያውቃሉና፡፡ በኵራት ስለ ክርስቶስ የሚያስተምሩ ግን፥ ይህን አደርገው በእስራቴ ላይ መከራ ሊጨምሩብኝ መስሏቸው ነው እንጂ በእውነት አይደለም፤ በቅንነትም አይደለም፡፡ ነገር ግን ምን አለ? በየምክንያቱ በእውነትም ቢኾን፥ በሐሰትም ቢኾን ስለ ክርስቶስ ይናገራሉ፤ ሰዉን ዂሉ ወደ እርሱ ይጠራሉ፡፡ በዚህም ደስ ብሎኛል፤ ወደ ፊትም ደስ ይለኛል፤› (ፊልጵ. ፩፥፲፭-፲፰) በማለት የክርስትና ተቃዋሚዎች ቅዱስ ጳውሎስን ለማሳሰርና በእርሱ ላይ ከባድ መከራ ለማምጣት ሲሉ ራሱ የሚሰብከውን ቅዱስ ወንጌል ለመጠቀም መጣራቸውን ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ገልጾልናል፡፡ ከመልእክቱ እንደምንረዳው ታላቁ ሐዋርያ በቅንዓትና በክፋትም ቢኾን ‹‹እሰይ! እንኳን ወንጌል ተሰበከ!›› ሲል ለበጎ አድርጎ ይወስደዋል፡፡ ድርጊታቸው ለበጎ ባይኾንም ሰማዕያንን ስለሚያዘጋጅለትና የበለጠ እንዲረዱ ስለሚጋብዝለት እንደ መልካም ዕድል ወስዶታል፤ ኾኖለታልም፡፡

እጅግ የሚያስደንቀው ደግሞ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እንቅፋት ይገጥመው የነበረው ቤተ ክርስቲያንን በሓላፊነት ሊያገለግሉ በተለያየ መዓርግ ከተሾሙት ወገኖች ጭምር መኾኑ ነበር፡፡ ይህም የተከሠተው ልክ እንደ ቀደመው ዂሉ ራሳቸው ሐዋርያት በነበሩበትና ከራሱ ከመድኃኔ ዓለም ክርስቶስ የሰሙትን የድኅነት ወንጌል በሚመሰክሩበት ዘመን ነበር፡፡ ከዚህም የተነሣ እንደ ፍቁረ እግዚእ ቅዱስ ዮሐንስ ያሉ ሐዋርያት ይሰሙናል ብለው ለሚያስቧቸው አገልጋዮች የሁለቱንም ዓይነት አገልጋዮች ጠቅሰው በጎውን እንዲመስሉና ክፉውን ግን እንዳይከተሉት ያሳስቡ እንደ ነበረ ለርእስነት ከተጠቀምንበት ኃይለ ቃል ለመረዳት ይቻላል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ ይህችን ሦስተኛዪቱን መልእክቱን የላካት ለደቀ መዝሙሩ ለጋይዮስ ሲኾን መልእክቱንና አደራውን የሚሰጠው በዘመኑ የነበሩትን ሁለቱንም ዓይነት አገልጋዮች በንጽጽር ካቀረበለት በኋላ ነበር፡፡ አንድ ምዕራፍ ብቻ ባላት፣ በይዘት አነስተኛ በኾነች፣ በጭብጥና በፍሬ ነገር ግን ከሌሎቹ መልእክታተ ሐዋርያት በማታንሰው በዚህች መልእክቱ ያነጻጸራቸው ሁለቱ አገልጋዮች ደግሞ ዲዮጥራጢስ እና ድሜጥሮስ ነበሩ፡፡

ሐዋርያው በዚህ መልእክቱ ቍጥር ዘጠኝ ላይ እንደ ገለጸው ዲዮጥራጢስ ፍቁረ እግዚእ የተባለ ቅዱስ ዮሐንስ ለቤተ ክርስቲያን የላከውን መልእክት እንኳን የማይቀበል፤ እንዲያገለግሉ የተፈቀደላቸውን አገልጋዮች የሚያንገላታና የሚቀበሏቸውን ሳይቀር ከቤተ ክርስቲያን ለማባረር ጥረት የሚያደርግ ክፉ አገልጋይ ነበረ፡፡ በአንጻሩ ድሜጥሮስ ደግሞ የቤተ ክርስቲያኒቱ የኾኑትን፣ ለዕድገቷና ለጥንካሬዋ የሚላላኩትን ዂሉ የሚቀበል፤ በመልካም የሚያስተናግድና ከበጎዎቹ ጋር ዂሉ አብሮ የሚሠራ፤ የልቡናውን ሳይኾን የቤተ ክርስቲያንን፤ የራሱን ብቻ ሳይኾን የአባቶቹን ድምፅ፣ ምክርና ዐሳብ ተቀብሎ የሚያስተናግድ ቅን አገልጋይ ነበር፡፡ ይህንንም ቅዱስ ዮሐንስ ‹‹ስለ ድሜጥሮስ ዂሉ ይመሰክሩለታል፤ እውነት ራሷም ትመሰክርለታለች፤ እኛም መስክረንለታል፤ ምስክርነታችንም እውነት እንደ ኾነች ታውቃላችሁ፤›› ሲል ይመሰክርታል (ቍ. ፲፪)፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ እነዚህን ሁለቱን አገልግዮች ያነጻጸረውም መልእክቱን የሚልክለት ሌላው ረድዕ ቅዱስ ጋይዮስ አብነት ሊያደርገው የሚገባው ዲዮጥራጢስን ሳይኾን ድሜጥሮስን መኾን እንዳለበት ለማሳየት ነው፡፡ ‹‹ወንድሜ ሆይ፥ በጎ አድራጊ እንጂ ክፉ አድራጊ አትኹን፤›› ማለቱም ስለዚህ ነው (ቍ. ፲፩)፡፡

በዘመናችን ያለው የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት የገጠመው ኹኔታም ከዚህ ኹኔታ ጋር በእጅጉ እንደሚመሳሰል ስለምናምን፤ ማኅበሩም ለአባላቱና ለወዳጆቹ ብቻ ሳይኾን በቤተ ክርስቲያን ላሉ አገልጋዮች ዂሉ የሚያቀርበው ወቅታዊ የአዘክሮ መልእክት ይኼው ‹‹ወንድሜ ሆይ፥ በጎ አድራጊ እንጂ ክፉ አድራጊ አትኹን፤›› የሚለው የቅዱስ ዮሐንስን ምክር ነው፡፡ የሐዋርያት ዘመን አገልግሎት በሁለቱ ዓይነት ሰዎች የተያዘ ከነበር የእኛ ዘመን አገልግሎት ከዚያ የተሻለ ነገር እንዴት ሊገጥመው ይችላል? ፍቁረ እግዚእ (ጌታ የሚወደው) የተባለው፤ በክርስቶስ ዕለተ ስቅለት እንኳን ከእግረ መስቀሉ ሳይርቅ ከመከራ መስቀሉ ያልሸሸው፤ እስከ ዕለተ ሞቱ ድረስም ሞተ ወልደ እግዚአብሔርን እያሰበ ፊቱን ለቅጽበትም ሳይፈታና ፈገግ ሳይል በፍጹም ዂለንተናው ያገለገለው፤ እኔ እስክመጣ ቢኖርስ ብሎ ጌታችን በቅርብ ሞትን እንደማያይ ቃል ኪዳን የገባለት፤ ንጽሕት ቅድስት ድንግል ማርያምን ‹‹እነኋት እናትህ›› ተብሎ ከእግረ መስቀል የተቀበለው ቅዱስ ዮሐንስ እስኪቸገር ድረስ ቤተ ክርስቲያንን ለፍላጎታቸው ብቻ የሚጠቀሙባት አገልጋዮች በዚያ ዘመን ከነበሩ ‹‹በእኛ ዘመን ለምን እንዲህ ያለ ነገር ኾነ?›› ብለን ልንደነቅበት የማይገባ እንደ ኾነ ለመረዳት የሚያስቸግር አይኾንም፡፡ በዚያው አንጻር ደግሞ እንደ ድሜጥሮስ እውነት ራሷ የምትመሰክርላቸው አገልጋዮች መኖራቸውን መዘንጋት ተገቢ አይደለም፡፡ ይልቁንስ ዋናውና ለእኛ ለዂላችን የሚያስፈልገው ነገር ‹‹እኛ ልንመስለውና አብነት ልናደርገው የሚገባው የትኛውን ነው?›› የሚለው ሊኾን ይገባል፡፡

የቍጥር መለያየትና የፍሬ ነገሩ መለዋወጥ ካልኾነ በቀር ዛሬም እንደ ጥንቱ ወይም በየዘመናቱ ዂሉ በታሪክ እንደ ተመዘገበው በቤተ ክርስቲያን ሁለቱም ዓይነት አገልጋዮች ይኖራሉ፡፡ ጌታችንም በወንጌል ‹‹ያን ጊዜ ሁለት ሰዎች በአንድ እርሻ ላይ ይኖራሉ፤ አንዱን ይወስዳሉ፤ ሁለተኛዉንም ይተዋሉ፡፡ ሁለት ሴቶች በአንድ ወፍጮ ይፈጫሉ፤ አንዲቱን ይወስዳሉ፤ ሁለተኛዪቱንም ይተዋሉ፡፡ ሁለት ሰዎች በአንድ አልጋ ላይ ይተኛሉ፤ አንዱን ይወስዳሉ፤ ሁለተኛዉንም ይተዋሉ፡፡ እንግዲህ ትጉ፤ ጌታችሁ በምን ሰዓት እንደሚመጣ አታውቁምና፤›› (ማቴ. ፳፬፥፵-፵፪) በማለት እስከ ዕለተ ምጽአት ድረስ ሁለቱም በእግዚአብሔር ቤት በአንድነት በአንድ የአገልግሎት መድረክ ላይ አንድ ዓይነት አገልግሎት እየፈጸሙ ለመኖራቸውና ለእግዚአብሔር የሚኾነውንና የማይኾነውን የሚለየውም እርሱ ራሱ በረቂቅ ፍርዱ እንደ ኾነ ገልጾልናል፡፡ ስለዚህም በአንዱ የወንጌል እርሻ ላይ እግዚአብሔር የሚወስደውና የሚተወው እንዳለ የሚያውቅ ባለቤቱ ስለ ገለጸልን የተጻፈውን ተረድተን፣ የጌታችንን ቃል ተቀብለን፣ በመኖሩ ከመደነቅ ወጥተን ልናደርገው ስለሚገባን ብቻ ማሰቡ ተገቢ ይኾናል፡፡ ቃሉ ዂላችንንም የሚመለከት የእውነትና የፍርድ ማስጠንቀቂያ ቃል ነውና፡፡

ስለዚህም በመግቢያው አንቀጽ ላይ እንደ ገለጽነው፣ ቅዱስ ጳውሎስን እንደ ገጠመው ዂሉ፣ በአሁኑ ጊዜም ወንጌልን ወይም ነገረ ቤተ ክርስቲያንን ለዓላማና ለጽድቅ የሚላላኩለት አሉ፤ በአንጻሩ ደግሞ እውነተኞቹን አጥፍቶ ፍላጎትን አንግሦ የራስን አጀንዳ ለማራመድ የሚሯሯጡትም አሉ፡፡ እነዚህም ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ገለጸው የንጹሐኑን አግልግሎት ሳይቀር አገልጋዮቹን ለመክሰስና ለመወንጀል በየዘመናቱ ከሚኖሩ የጥፋት አካላት ጋር ወዳጅነትን ለመግዛትና ለመሳሰሉት ይጠቀሙበታል፤ ሕዝብንም ለመቀስቀስና ከራሳቸው ጋር ለማሰለፍ ይሠሩበታል፤ መልካሙን ነገር ለክፉና ለጥፋት እየተረጐሙ ያቀርቡበታል ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስን እንደ ገጠመውም ከቤተ ክርስቲያን ፍላጎት፣ ከሐዋርያት እና ከተላውያነ ሐዋርያት (ከሐዋርያት ተከታዮች) በጎ ምክር ይልቅ የራሳቸውን እና የእኔ የሚሉትን አካል ጥቅም ለማስጠበቅ ብቻ ሊጠቀሙበት ይደክማሉ፡፡ ይህ የየዘመኑ ክሥተት እንደ ኾነው ዂሉ የእኛም ዘመን ትንሽና ደካማ አገልግሎት እንኳን ከዚህ ልታመልጥ አልቻለችም፡፡ ምንም እንኳን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለፊልጵስዩስ ክርስቲያኖች ‹‹የእነርሱ ጥፋት፥ የእናንተም ሕይወት ይታወቅ ዘንድ የሚቃወሙን ሰዎች በማናቸውም አያስደንግጧችሁ፡፡ ይህንም ጸጋ እግዚአብሔር ሰጥቷችኋል፤ ነገር ግን ስለ እርሱ መከራ ልትቀበሉም ነው እንጂ ልታምኑበት ብቻ አይደለም፤›› (ፊልጵ. ፩፥፳፰-፳፱) ሲል እንደ ገለጸው የማይቀርና ዂሉም ነገር ልንቀበለው የሚገባ ቢኾንም አንዳንድ ጊዜ ግን ነገሩን ከሃይማኖት አንጻር ከማየት ወጥተን እንዳንገኝ ራስን መመርመሩ በእጅጉ የተገባ ነው፡፡

ምንም እንኳን ግብሩና ስሙ ብዙ የተራራቁ እንደ ኾኑ ጥናቶች ቢያመለክቱም የእኛ ዘመን የመረጃ ዘመን ነው ስለሚባል ኢንተርኔትን ተጠቅሞ በዋና መገናኛ ብዙኃንም ኾነ በየማኅበራዊ ሚዲያው የሚሠራጨውን ዂሉ አምኖና ተቀብሎ መሔድ ሳናውቀውም ቢኾን ወሬ ፈጣሪዎቹንና የጥፋት መልእክት አሠራጮችን ከመምሰል የሚያድን አይደለም፡፡ በማኅበራችን በማኅበረ ቅዱሳን ስም የሚሠራጩ አስመስለው ለሚከስሱና ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ተናገረው ለተንኮልና መከራ ለመጎተት ኾነ ብለው የሚሠሩትን ከመተባበርም፣ ለይቶ ለማየትም አስቸጋሪ ደረጃ ላይ እንደ ደረሰ ለብዙዎች አያዳግትም፡፡ ማኅበሩ አቋሙን፣ መልእክቶቹንና ለሕዝበ ክርስቲያን ሊደርሱ ይገባቸዋል የሚላቸውን መረጃዎች ዂሉ በራሱ ይፋዊ ሚዲያዎች ወይም ደግሞ ማኅበሩን በሕግ በሚወክሉ አካላት የሚዲያ መግለጫዎች ብቻ የሚገልጽ ቢኾንም አንዳንዶች ግን እነዚህን ዂሉ ሳያጠሩና ሳይመረምሩ በማኅበሩ ስም ለክስ የሚያመቹ አድርገው የሚጽፉ አካላትን መረጃዎች በማኅበራዊ ሚዲያ ሳይቀር እንደሚቀባበሉ፤ የማኅበሩን አገልግሎትና አሠራር ከሚረዱት ምእመናን የሚደርሱት ጥቆማዎች ያመለክታሉ፡፡

ስለዚህም ኾነ ብላችሁና በተንኮልም ባይኾን የማኅበሩ መልእክቶችና አቋሞች መኾናቸውን ከማኅበሩ አካላት ሳትጠይቁና ሳትረዱ፤ ነገሩንም ሳትመረምሩ በችኮላና በስሜት ምን አልባትም ከዚህ በፊት በነበራችሁ የተሳሳተ መረጃና ግምት ምክንያት ለተጻፉና በማኅበራዊ ሚዲያው በሚናፈሱት ዂሉ ማኅበሩን ለምትወቅሱ፣ ለምትተቹና ለምትሰድቡም ዂሉ ወደ ማኅበሩ ቀርባችሁ ኹኔታዎቹን ሳታጣሩና መረጃ ሳትቀበሉ መዘገባችሁን እንድታቆሙ ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡ ቢያንስ ቢያንስ የሙያ ሥነ ምግባሩ የሚጠይቀውን ያህል እንኳ ሳትጓዙ ለመፈረጅ መቻኮላችሁ የሚያስገርም ኾኖም አግኝተነዋል፤ በሌላው ላይ የማታደርጉትን ማደረጋችሁን በግልጽ ያመለክታልና፡፡ አውቃችሁና ወዳጅ መስላችሁ ለራሳችሁ የተንኮልና የክስ ዓላማ እንዲጠቅማችሁ በማሰብ ይህን በማኅበሩ፣ በአባላቱና በወዳጆቹ ስም ስማቸው በይፋ በማይታወቁ አካላት ስም ይህን የምታደርጉትንም ቢኾን አይጠቅማችሁምና ከዚህ ድርጊታችሁ እንድትታቀቡ እውነትና ፍቅር በኾነው አምላካችን ስም እናሳስባችኋለን፡፡ ባለማወቅ እና ለማኅበሩ አገልግሎት የሚያግዝ እየመሰላችሁ ይህን የምታደርጉ አባላትም ኾነ ደጋፊዎች ካላችሁም እንደሚባሉት ያሉ የስድብና የጥላቻ መልእክቶች ማኅበሩን ሊጠቅሙ ቀርቶ የአገልግሎቱ አደናቃፊዎችንም ሊጎዱ ስለማይችሉ፤ ሊጎዱ እንኳ ቢችሉ በክርስትናችን የተከለከሉና የተወገዙ ስለ ኾኑ ከማድረግ እንድትቆጠቡ ለማሳሰብ፣ በሐዋርያው ቃልም  ‹‹ወንድሜ ሆይ፥ በጎ አድራጊ እንጂ ክፉ አድራጊ አትኹን፤››  ለማለት እንወዳለን፡፡

የማኅበሩ አባላትና ወዳጆቹ፣ እንዲሁም የአገልግሎት አጋሮቹና ተባባሪዎቹ ዂላችሁ በቅዱሳት መጻሕፍት የተጻፉልንን ምክሮች ከማዘከርና ዂልጊዜም ቢኾን ከክፉው ተጠብቀን መልካም የኾነውን አርአያና አብነት ከማድረግ ልንቆጠብ አይገባንም፡፡ በትንሹ እና ሕይወታችንን በሙሉ ሳይኾን ከትርፋችን የምናገለግላት ቤተ ክርስቲያናችን በምድር ላይ እንዳሉ ሌሎች ተቋማት የዚህ ዓለም አደረጃጀትና አሠራር ብቻ የሚመራት ምድራዊ ተቋም ሳትኾን ረቂቅነትን እና መንፈሳዊነትንም ገንዘብ ያደረገች አካለ ክርስቶስ እንደ መኾኗ መጠን የምንፈጽመው ዂሉ መንፈሳዊነት ከጎደለው፣ ርባና ቢስ መኾኑን ለአፍታም ቢኾን ልንዘነጋው የሚገባ ነገር አይደለም፡፡ ለድርጊቶቻችን አብነት የምናደርገውም ቅዱስ ዮሐንስ እንዳስተማረው ብልሆቹን፣  መልካሞቹንና ደጎቹን እንጂ ሞኞቹን፣ ክፉዎቹንና ተንኮለኞቹን ሊኾን አይችልም፡፡ በዚያውም ላይ ከቅዱሳት መጻሕፍት ምክር ልንወጣ አይፈቀድልንም፡፡ ራሱ ጌታችን ‹‹ብትወዱኝስ ትእዛዜን ጠብቁ›› አለን እንጂ የተቃዋሚዎቻችን ሰይፍና ጎመድ ልንይዝ አልፈቀደልንም፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹ወገኖቻችንም ፍሬ ቢሶች እንዳይኾኑ፥ በሚፈለገውም ሥራ ጸንተው እንዲገኙ በጎ ምግባርን ይማሩ፤›› (ቲቶ. ፫፥፲፬) በማለት እንደ ገለጸው ከቤተ ክርስቲያን ወገን የኾናችሁ ዂሉ፣ በውጭ እንዳሉት ወደ ፍሬ ቢስነት ከሚወስድ ማንኛውም መንገድ ልትቆጠቡ ይገባችኋል፡፡

በእርግጥ ነቢየ እግዚአብሔር ኤርምያስ ‹‹በሕዝቤ መካከል ክፉዎች ሰዎች ተገኝተዋል፤ ሰዎችንም ይዘው ይገድሉ ዘንድ ወጥመድን ይዘረጋሉ፤›› (ኤር. ፭፥፳፮) ሲል እንዳመለከተን፣ በመካከል የተዘሩ አጥማጆችና ባለ ወጥመዶች ሊያሰነካክሉን፣ ስሜታችንን ሊያደፈርሱትና ወደ ወጥመዳቸው ሊያንደርድሩን በተለያየ ዘዴ ይገፉን ይኾናል፡፡ ኾኖም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ ‹‹ነገር ግን ወንድሞች ሆይ፥ ትበዙና ትጨምሩ ዘንድ እንማልዳችኋለን፡፡  የዋሃንም ትኾኑ ዘንድ፥ ሥራችሁንም ታከናውኑ ዘንድ፥ እንዳዘዝናችሁም በእጃችሁ ትሠሩ ዘንድ፥ በውጭ ባሉት ሰዎችም ዘንድ ከማንም አንዳች ሳትሹ በሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እንለምናችኋለን፤›› (፩ኛ ተሰ. ፬፥፲-፲፪) ሲል ያዘዘንን ቃል ማስታወስ አስፈላጊ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም ‹‹ፍጹም ዋጋ እንድታገኙ እንጂ የሠራችሁበትን እንዳታጡ ራሳችሁን ዕወቁ፤›› (፪ኛ ዮሐ. ቍ. ፰) በማለት እንደዚህ ዓይነት ክፉ ተግባር የቀደመ መልካም ተግባራችንን ዋጋ ጨምሮ የሚያጠፋ መኾኑን በማስታወስ ፈጽመን እንዳናደርገው ያስጠነቅቀናል፡፡ ምንም ያህል ፈተና እና መከራ ቢመጣም እኛ ልናደርገው የሚገባን በመልካም ሥራና ልናደርገው የሚገባውን በማደረግ መጽናት ብቻ ይኾናል፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹በእግዚአብሔር የሚያምኑ ሰዎች በመልካም ምግባር ዂሉ መረዳዳትን እንዲያስቡ ታጸናቸው ዘንድ እወዳለሁ፤ ሰውንም የሚጠቅመው በጎ ነገር ይህ ነው፤›› (ቲቶ ፫፥፰) ሲል ለቲቶ ያሳሰበውና ለዂላችንም የደረሰው፣ ጥቅም የሚገኘው በመንፈሳዊነትና በእውነት ኾኖ በመጽናት ብቻ ስለ ኾነ ነው፡፡

አንዳንድ ጊዜ እንዲህ ያለውን ምክር የማይቀበሉና በራሳቸው ዐሳብ ሔደው ለቤተ ክርስቲያን ጥቅምና ረብ ማስገኘት የሚችሉ አስመስለው የሚናገሩ፤ ዐሳባቸውንም በአንዳንድ ጥቅሶች አስደግፈው በተቆርቋሪነት መንፈስ የሚገዳደሩአችሁ እንኳን ቢኖሩ፣ እንዲህ ያለውንም ፈተና በትዕግሥት እንድትወጡትና አሁንም በጎውን እንድትመርጡ እናሳስባችኋለን፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹‹እግዚአብሔር ወገኖቹን ያውቃቸዋል፤ የእግዚአብሔርንም ስም የሚጠራ ዂሉ ከክፉ ነገር ይርቃል› የሚለው ይህም ማኅተም ያለበት የእግዚአብሔር መሠረት ጸንቶ ይቆማል፤›› (፪ኛ ጢሞ. ፪፥፲፱) በማለት ለቅዱስ ጢሞቴዎስ ያሳሰበውም በእግዚአብሔር እና በቤተ ክርስቲያን ስም ሰዎች ያልተገባ ድርጊት ውስጥ እንዳይገቡ ለማስጠንቀቅ ነውና፡፡ ሐዋርያው እንደዚህ ያሉትን ሰዎች ከዚህም አለፍ ብሎ ‹‹እግዚአብሔርን እንደሚያውቁት በግልጥ ይናገራሉ፤ በሥራቸው ግን ይክዱታል፤ እነርሱም ርኩሳንና የማይታዘዙ፥ በበጎ ሥራም ዂሉ የተናቁ ናቸው፤›› (ቲቶ ፩፥፲፮) በማለት ድርጊታቸውን ከክህደት ይደምረዋል እንጂ ተቆርቋሪዎች ብሎ አያመሰግናቸውም፡፡ ይህን እውነት ተረድተናል የምንል ደግሞ ‹‹አሁንም ስለዚህ እናንተ እንደምታደርጉ ወንድሞቻችሁን አጽናኑ፡፡ አንዱም አንዱም ወንድሙን ያንጸው (፩ኛ ተሰ. ፭፥፲፩) በተባለው ቃል ተጠቅመን ልንተራረም እንጂ ልንተቻች አይገባንም፡፡ ቢቻል ቢቻል ‹‹ያን ጊዜም አለቆችና መሳፍንቱ ስለ መንግሥቱ በዳንኤል ላይ ምክንያት ይፈልጉ ነበር፤ ነገር ግን የታመነ ነበርና፥ ምንም በደል አልተገኘበትምና በእርሱ ላይ ሰበብና በደል ያገኙበት ዘንድ አልቻሉም፤››  (ዳን. ፮፥፬-፭) ተብሎ እንደ ተመሰከረለት እንደ ዳንኤል ሰበብ የለሽ እስከ መኾን መድረስ፤ ካልተቻለ ደግሞ ሊያስፈርድብን ከሚገባ ስሕተትና ጥፋት መቆጠብ ለክርስቲያን ዂሉ የሚገባው ተግባር ነው፡፡

ይህ ዂሉ ግን ክሶችንና ውንጀላዎችን ያስቀራል ማለት እንዳልኾነ የተጠቀሱት ጥቅሶች ለመጻፋቸው ምክንያት ከኾኑት ታሪኮች፣ ይልቁንም ከነቢዩ ዳንኤል ታሪክ የምንረዳው ነው፡፡ ኾኖም ክርስቲያኖች ይህን ዂሉ ሊያደርጉት የሚገባቸው በሌላ በምንም ምክንያት ሳይኾን ‹‹ነገር ግን እግዚአብሔር ስለ ፈተነንና ወንጌሉን ለማስተማር የታመን ስላደረገን እንዲህ እናስተምራለን፤ ሰውን ደስ ለማሰኘት እንደሚሠራም አይደለም፤ ልቡናችንን ለመረመረው ለእግዚአብሔር ነው እንጂ፤›› (፩ኛ ተሰ. ፪፥፬) ተብሎ እንደ ተጻፈው አገልግሎታችን እናገለግልሃለን የምንለውን እግዚአብሔርን ደስ ስለማሰኘት ብቻ ነው፡፡ ማኅበሩም ቢኾን ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ ‹‹ልጆቼ በእውነት ሲሔዱ ከመስማት ይልቅ ከዚች የምትበልጥ ደስታ የለችኝም፤›› (፫ኛ ዮሐ. ቍ. ፬) ሲል እንደ ገለጸው አባላቱና ደጋፊዎቹ ብቻ ሳይኾኑ ክርስቲያኖች ዂሉ በእውነት ሲሔዱ ከማየት የተለየ ፍላጎት የለውም፡፡ ስለዚህም ይህ መልእክት የደረሳቸውንም ዂሉ ከታዘዙት በበለጠ እንዲፈጽሙት ይበረቱ ዘንድ ‹‹በመታዘዝህ ታምኜ፥ ካዘዝኹህም ይልቅ እንደምትጨምር ዐውቄ ጻፍኹልህ፤›› (ፊልሞና ፩፥፳፩) የሚለውን ቃለ ሐዋርያ እያስታወስን፤ በቃለ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ በድጋሜ ‹‹ወንድሜ፣ ወዳጄ (አባል፣ ደጋፊ፣ ተባባሪ፣ ክርስቲያን ዂሉ) ሆይ፥ በጎ አድራጊ እንጂ ክፉ አድራጊ አትኹን›› በማለት ማኅበረ ቅዱሳን መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር!

ማኅበረ ቅዱሳን