የስብከተ ወንጌል አገልግሎቱንና ሰባክያኑን እንደግፍ

በገጠርና ጠረፋማ አካባቢዎች የሚያገለግሉ ሰባክያነ ወንጌል

በገጠርና ጠረፋማው የአገራችን ክፍል ተበታትነው የሚኖሩ ብዙ ወገኖቻችን እውነተኛውን የወንጌል ብርሃን ሳይመለከቱ፣ ለሥላሴ ልጅነት ሳይበቁ፣ በጎውን ነገር ሳያዩ፣ ድኅነትን እንደ ናፈቁ ሞተ ሥጋ ይቀድማቸዋል፡፡

ጥቂት የእግዚአብሔርን ቃል ያወቁ ወንድሞች የምሥራቹን የእግዚአብሔርን ቃል ለማብሠር፤ ለወገኖቻቸው የወንጌል ብርሃንን ፈንጥቀው ወደ ዘላለማዊ ሕይወት ለማሸጋገር ሲሉ የበረኃው ንዳድ፣ የአራዊቱ ግርማ፣ ረኃቡና ጥሙ፣ ስቃዩና ሕመሙ ሳይበግራቸው፣ እንቅልፍ በዐይናቸው ሳይዞር የሐዋርያትን አሰር ተከትለው ከጠረፍ ጠረፍ እየተዘዋወሩ ወንጌልን ይሰብካሉ፡፡

የእናት ቤተ ክርስቲያናቸውን ርእይ በማንገብ ለወገኖቻቸው በጥምቀት የሥላሴ ልጅነትን ለማሰጠት ለቀናት በረኃውን በእግር ያቋርጣሉ፤ እነርሱ በእግር ሁለት፣ ሦስት ቀን የሚወጡ የሚወርዱበትን መንገድ ሌሎች የጥፋት መልእክተኞች (መናፍቃን) በዘመናዊ ተሽከርካሪ ገደል ኮረብታውን ጥሰው፣ በግል ሄሊኮፕተር ጭምር ያለ ችግር ቀድመው በመድረሳቸው ብቻ ወገኖቻችንን ይነጥቃሉ፤ ያልዘሩትን ያጭዳሉ፡፡ ይህም ለእኛ ሰባክያነ ወንጌል ሌላ ድካም ይኾንባቸዋል፤ ቀድመው ባለ መድረሳቸው በወገኖቻቸው ላይ የተዘራውን ክፉ አረም ለመንቀል ጊዜም ጕልበትም ይፈጃልና፡፡

እነዚያ የበረኃ ሐዋርያት ‹‹ወልድ ዋሕድ›› ብለው ሲያስተምሯቸው፣ ስለ ቅዱሳኑ ምልጃ ሲነግሯቸው፣ የእግዚአብሔርን መንግሥት መውረሻ ስለኾነችው ዳግም ልጅነትን ስለምታሰጠው አሐቲ ጥምቀት ሲያበሥሯቸው ‹‹እስከዚህ ዕድሜያችን ድረስ ስንጠብቃችሁ ነበር፤ እኛ የምናምነው አያቶቻችን የነገሩንን የቄሶች ሃይማኖት ነው፡፡ አስተምሩን፤ አጥምቁን፤›› ይሏቸዋል፡፡

ሰባክያኑ ከዚህ ያለውን አረም ነቅለው ሌሎች ወገኖቻቸው ጋር ለመድረስ ሲነሡ በክንፍ አይበሩ ነገር እንዴት ይድረሱ? ሥጋ ለባሽ ናቸውና ከመንገድ ይመለሳሉ፡፡ እነዚህ የበረኃ ሐዋርያት በአንዲት ሞተር ሳይክል እጦት ምክንያት በጊንጥና በእባብ እየተነደፉ፣ አጋዥ አጥተው ለወገኖቻቸው ቃለ ወንጌልን ሳያዳርሱ ይቀራሉ፡፡

እነዚህ ሐዋርያት ያለምንም እገዛ በረኃውን በእግር እያቋረጡ ከ፹፮ ሺሕ በላይ ወገኖችን በጥምቀት የሥላሴ ልጅነትን እንዲያገኙ ማድረግ ከተቻላቸው፣ ድካማቸውን በትንሹም ቢኾን ብንቀንስላቸው ደግሞ በመቶ ሺሕ የሚቈጠሩ ወገኖችን እንደሚያስጠምቁ የታመነ ነው፡፡

በጕዞ የደከመ የሰባክያኑን ጕልበት ለማደስ ፍቱን መድኀኒቱ ሞተር ሳይክል ነውና እኛ ከቤታችን ኾነን በጕዞ ሳንደክም አንዲት ሞተር ሳይክል በመለገስ ተራራውንና ቁልቁለቱን፣ በረኃውንና ቁሩን ከሐዋርያቱ ጋር አብረን እንውጣ፤ እንውረድ፡፡ የስብከተ ወንጌል አገልግሎቱንና ሰባክያኑን በመደገፍ የበረከቱ ተሳታፊዎች እንኹን፡፡

ሞተር

በጎ አድራጊው ምእመን የሞተር ሳይክል ስጦታ ሲያበረክቱ

ለድጋፋችሁና ሐሳቦቻችሁ በ 09 60 67 67 67 ደውሉልን

በማኅበረ ቅዱሳን የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብር

ልደተ ስምዖን ነቢይ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የካቲት ፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! ጥር ፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ‹‹በዓለ ግዝረት›› በሚል ርእስ ባቀረብነው ትምህርታዊ ጽሑፍ ነቢዩ ስምዖን ጌታችንን እንደ ታቀፈውና ከእርግናው እንደ ታደሰ፤ ከክርስቶስ ቤዛነት ጋር የተያያዘ ትንቢት እንደ ተናገረ፤ ነቢዪት ሐናም የክርስቶስን የማዳን ሥራ ለሕዝቡ ዅሉ እንደ መሰከረች መግለጻችን ይታወሳል፡፡ ኾኖም ግን ይህ ታሪክ የሚነገረው ጌታችን ሥርዓተ ግዝረትን በፈጸመበት ዕለት (ጥር ፮ ቀን) ሳይኾን ጌታችን ወደ ቤተ መቅደስ በገባበት ዕለት (የካቲት ፰ ቀን) መኾኑን እንድትገነዘቡልን በትሕትና እያሳሰብን ወደ ዛሬው ዝግጅታችን እንወስዳችኋለን፤

በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ የካቲት ፰ ቀን ከሚከበሩ በዓላት መካከል የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቤተ መቅደስ መግባት፣ የነቢዩ ስምዖን ልደት (መታደስ) እና የነቢዪት ሐና ዕረፍት በስፋት ይነገራል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደ በስምንተኛው ቀን (ጥር ፮ ቀን) በኦሪቱ ሕግ መሠረት ሥርዓተ ግዝረትን ፈጽሟል፡፡ በተወለደ በዐርባኛ ቀኑ (የካቲት ፰ ቀን) ደግሞ ወደ ቤተ መቅደስ ገብቷል፡፡ (ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተወለደበት ከታኅሣሥ ፳፱ ቀን ጀምረን ስንቈጥር  የካቲት ፰ ዐርባኛው ቀን ነው፡፡)

በቅዱስ ወንጌል እንደ ተመዘገበው ከሕርስ ደም የሚነጹበት ጊዜ ሲደርስ ‹‹የእናቱን ማኅፀን የሚከፍት ወንድ (የበኵር ልጅ) ዅሉ ለጌታ የተቀደሰ ይባላል›› ተብሎ እንደ ተጻፈ እንደ ኦሪቱ ሥርዓት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እና ጠባቂዋ ጻድቁ ዮሴፍ ለመሥዋዕት የሚቀርቡ እንስሳትን ይዘው ጌታችንን በዚህች ዕለት ወደ ቤተ መቅደስ ወሰዱት፡፡ ‹‹ከሕርስ ደም የሚነጹበት ጊዜ ሲደርስ›› ሲልም በሌሎች ሴቶች ልማድ ለመናገር ነው እንጂ በእመቤታችንስ ይህ ዅሉ ጣጣ የለባትም፡፡ ከሴቶች ተለይታ የተመረጠች ቅድስት የአምላክ እናት እንደ መኾኗ ለድንግል ማርያም ርስሐት በፍጹም አይስማማትም፡፡ በሌላ በኩል ‹‹ከሕርስ ደም የሚነጹበት ጊዜ ሲደርስ›› ማለት ከሰው የሚለዩበትን ጊዜ ያመለክታል፡፡ ወንዶች በተወለዱ በዐርባ፣ ሴቶች በሰማንያ ቀናቸው ከሰው ይለያሉና፡፡

ጌታችን ወደ ቤተ መቅደስ በሔደ ጊዜም አረጋዊው ነቢዩ ስምዖን ታቅፎት ሰውነቱ ታድሷል፡፡ ይህ ዕለት (የካቲት ፰ ቀን) ‹‹ልደተ ስምዖን›› እየተባለ የሚጠራውም ዕለቱ ነቢዩ ጌታችንን ታቅፎ ከእርግናው (ሽምግልናው) የታደሰበት፤ ከደዌው የተፈወሰበት፤ አምላኩን በሥጋ ያየበት በአጠቃላይ ዳግም የተወለደበት ዕለት በመኾኑ ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ‹‹ስምዖን›› በሚለው ስም ከሚጠሩ ቅዱሳን መካከል ነቢዩ ስምዖን አንዱ ነው፡፡ የነቢዩን ታሪክ ለማስታዎስ ያህል አባታችን አዳም በተፈጠረ በአምስት ሺሕ ሁለት መቶ ዓመት በንጉሥ በጥሊሞስ ዘመነ መንግሥት የኦሪት መጻሕፍትን ከዕብራይስጥ ወደ ጽርዕ (ግሪክ) ቋንቋ እንዲተረጕሙ ከታዘዙ ሰብዓ ሰዎች (ሊቃናት) መካከል አንዱ ነቢዩ ስምዖን ነው፡፡

ይህ ነቢይ ትንቢተ ኢሳይያስ ደረሰውና እየተረጐመ ሳለ ‹‹እነሆ ድንግል ትፀንሳለች፤ ወንድ ልጅንም ትወልዳለች፡፡ ስሙንም ዐማኑኤል ትለዋለች፤›› ከሚለው ኀይለ ቃል በደረሰ ጊዜ በቀጥታ ቢተረጕመው ንጉሡ እንደማይቀበለው በማሰቡ፤ እርሱም ‹‹ይህ እንዴት ሊኾን ይችላል?›› ብሎ በመጠራጠሩ ‹‹ድንግል›› የሚለውን ቃል ‹‹ወለት›› (ሴት ልጅ) ብሎ ተረጐመው፡፡ ተኝቶ በነቃ ጊዜም ‹‹ወለት›› የሚለው ቃል ተፍቆ ‹‹ድንግል›› ተብሎ ተጽፎ አገኘና እርሱም ‹‹ድንግል››ን ፍቆ ‹‹ወለት›› ብሎ ይጽፋል፡፡ ዳግመኛም ለሁለተኛና ጊዜ ተኝቶ ሲነቃ ቃሉ እንደ ነበረ ኾኖ ያገኘዋል፡፡ ለሦስተኛ ጊዜ ቃሉን እፍቃለሁ ሲልም የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጦ ‹‹የተጠራጠርኸውን፣ ከድንግል የሚወለደው ክርስቶስን እስከምታየውና እስከምትታቀፈው ድረስ ሞትን አትቀምስም፤›› ብሎታል፡፡

‹‹መሲሑን ሳታይ አትሞት›› የተባለው ነቢዩ ስምዖን አርጅቶ ከአልጋ ተጣብቆ ለሦስት መቶ ዓመታት ያህል ከኖረ በኋላ ትንቢቱ ተፈጽሞ፣ ዘመኑ ደርሶ ክርስቶስ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደ በዐርባኛው ቀን ወደ ቤተ መቅደስ እስከ በገባበት ዕለት መንፈስ ቅዱስ አነሳሥቶ ወደ ምኵራብ ወሰደው፡፡ በዚያም ጌታችንን ከእመቤታችን ተቀብሎ ለመታቀፍ ታድሏል፡፡ ‹‹የምትጠብቀው ሕፃን ይህ ነው›› ብሎ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በነገረው ጊዜም ታውረው የነበሩ ዓይኖቹ ተገልጠዋል፤ ሰውነቱም ታደሷል፡፡

ነቢዩም የእግዚአብሔርን ማዳን በዓይኑ በማየቱ፣ ከደዌው በመፈወሱ እና ከእርጅናው በመታደሱ በአጠቃላይ በተደረገለት ድንቅ ተአምር ዅሉ በመደሰቱ እግዚአብሔርን አመስግኗል፡፡ ‹‹አቤቱ ባሪያህን ዛሬ አሰናብተኝ፤ ዓይኖቼ ትድግናህን አይተዋልና፤›› በሚለው ትንቢታዊ መዝሙሩም ‹‹የእግዚአብሔርን ማዳን በዓይኔ ስላየሁ እንግዲህስ ልረፍ›› በማለት ሞቱን ተማጽኗል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶም የክርስቶስን የዓለም ቤዛነትና ክርስቶስ በሥጋው በሚቀበለው መከራ እመቤታችን መራራ ኀዘን እንደሚደርስባት፤ እንደዚሁም ጌታችን ለሚያምኑበት ድኅነትን፣ ለሚክዱት ደግሞ ሞትን የሚያመጣ አምላክ እንደ ኾነ የሚያስገነዝብ ትንቢት ተናግሯል፡፡

የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ለነቢዩ ስምዖን የተደረገለትን ታላቅ ሥራ ሲያደንቁ እንዲህ ይገልጹታል፤ ‹‹ሰላም እብል እንዘ እዌድሶ ወእንዕዶ፤ መዝሙረ ማኅሌት በአስተዋድዶ፤ ክብረ ስምዖን ነቢይ ለክብረ ሱራፌል ዘይፈደፍዶ፤ እስመ ሐቀፈ መለኮተ ወገሠሠ ነዶ፤ እኤምኅ ሕፅኖ ወእስዕም እዶ፤ የማኅሌት መዝሙርን በማዘጋጀት እያከበርሁትና እያደነቅሁት ከሱራፌል ክብር ለሚበልጠው ለስምዖን ክብር ሰላም እላለሁ፡፡ እርሱ መለኮትን በእጁ ታቅፏል፤ እሳቱንም ዳሷልና እቅፎቹን እጅ እነሳለሁ፤ እጆቹንም እስማለሁ፤›› /መጽሐፈ ስንክሳር፣ የየካቲት ፰ ቀን አርኬ/፡፡ የዚህ አርኬ መልእክት ኪሩቤል፣ ሱራፌል (ሰማያውያን መላእክት) በእጃቸው የማይነኩት፣ ከግርማው የተነሣ የሚንቀጠቀጡለት፣ እሳተ መለኮቱ የሚቃጥል እግዚአብሔር ወልድን ነቢዩ ስምዖን በክንዱ ለመታቀፍ በመታደሉ ክብሩ ከመላእክት እንደሚበልጥ፤ ለክብሩም የጸጋ ምስጋና እና እጅ መንሻ ማቅረብ እንደሚገባ የሚያስገነዝብ ነው፡፡

በተመሳሳይ መልኩ የነቢዪት ሐና ዕፍትም በዛሬው ዕለት ይታሰባል፡፡ ይህቺ ቅድስት ከአሴር ነገድ የተገኘች ደግ እናት ስትኾን አባቷም ፋኑኤል ይባላል፡፡ ክብረ ንጽሕናዋን ጠብቃ በድንግልና ኾና ዐሥራ አምስት ዓመት ሲሞላት ባል አግብታ ሰባት ዓመት ከባሏ ጋር ቆይታለች፡፡ ከባሏ ጋር ከተፋታች በኋላ ራሷን ጠብቃ ቀንም ሌትም ከምኵራብ ሳትወጣ በጾም በጸሎት ተወስና በሚቻላት ዅሉ እግዚአብሔርን እያገለገለች ሰማንያ አራት ዓመት ኖራለች፡፡ ይህቺ የአንድ መቶ ስድስት ዓመቷ አረጋዊት ጌታችን ወደ ቤተ መቅደስ በገባበት ዕለት በምኵራብ ተገኝታ አምላኳን በዓይኗ ለማየት በማታደሏ በክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅነት እና የዓለም ቤዛነት አመነች፡፡ ለዚህ ቀን ያደረሳትን እግዚአብሔርንም አመሰገነች፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝታም የክርስቶስን ሥራ እያደነቀች የሰውን ድኅነት በተስፋ ለሚጠባበቁ ለኢየሩሳሌም ሕዝቦች አዳኝነቱን መሰከረች /ሉቃ.፪፥፴፮-፴፱/፡፡ በመጨረሻም በዛሬው ዕለት ዐርፋለች፡፡

ምንጭ፡-

መጽሐፈ ስንክሳር፣ የካቲት ፰ ቀን፡፡

የሉቃስ ወንጌል አንድምታ ትርጓሜ፣ ሉቃ.፪፥፳፪-፴፱፡፡

ከዚህ ታሪክ ከምንገነዘባቸው በርካታ ቁም ነገሮች መካከል ጥቂቱን ለመጥቀስ ያህል ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሦስቱ አካላት (አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ) አንዱ (ወልድ) ነው፡፡ እንደ አምላክነቱ በዅሉም ቦታ የመላ ነውና መሔድ መምጣት፣ መራብ መጠማት የባሕርዩ አይደለም፡፡ ስለዚህም ‹‹ሔደ፤ መጣ፤ ተራበ፤ ተጠማ፤ ተገረዘ፤ ወደ ቤተ መቅደስ ሔደ፤ ወዘተ.›› የመሳሰሉ ለፍጡራን የሚስማሙ ቃላት አይነገሩለትም፡፡ ነገር ግን መድኀኒታችን ክርስቶስ መገረዝ፣ መሔድ፣ መምጣት፣ መራብ፣ መጠማት የሚስማማው ሥጋን ለብሷልና የሰውነቱን ሥራ ይፈጽም ዘንድ በመጽሐፍ ቅዱስ በተቀመጠው ሕግ መሠረት በተወለደ በስምንተኛው ቀን ለመገረዝ፤ በዐርባኛው ቀን ደግሞ ለመቀደስ (መሥዋዕት ለማቅረብ) ወደ ቤተ መቅደስ ሔዷል፡፡ ከዚህም እርሱ አምላክ ነኝ እና በተአምራቴ የማዳን ሥራዬን ልፈጽም ሳይል ከኀጢአትና ከፈቃደ ሥጋ በስተቀር በሰው ሥርዓት ማደጉን፤ እንደዚሁም የትሕትና ጌታ መኾኑን እንማራለን፡፡ ዛሬም ምእመናን ልጅ ሲወልዱ ወንዶችን በዐርባ፤ ሴቶች ደግሞ በሰማንያ ቀን ወደ ቤተ ክርስቲያን በመውሰድ ክርስትና የሚያስነሡት በዚህ ሥርዓት መሠረት ነው፡፡

ከነቢዩ ስምዖን ታሪክም በመጀመሪያ እግዚአብሔር አምላክ የማይፈጽመውን የማይናገር፤ የተናገረውንም የማያስቀር የእውነት ባለቤት እንደ ኾነ፤ እንደዚሁም እኛ አይደረግም ያልነው ከባድ የሚመስለን ምሥጢር ጊዜውን ጠብቆ መፈጸሙ እንደማይቀር፤ በተጨማሪም እግዚአብሔር በጥበብ የሚገሥፅ፣ የሚያስተምር የፍቅር አምላክ እንደ ኾነ እንገነዘባለን፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም በሥርዓተ ጋብቻ እስኪወሰኑ ድረስ ወንድሞችም እኅቶችም ክብረ ንፅሕናቸውን ጠብቀው መቆየት እንዳለባቸው፤ ከጋብቻ በኋላ ከሁለቱ ጥንዶች አንዱ በሞት ቢለይ ፈቃደ ሥጋቸውን መግታትና ሰውነታቸውን መቈጣጠር የሚቻላቸው ከኾነ እስከ ምድራዊ ሕይወታቸው ፍጻሜ ራሳቸውን ጠብቀው እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ ቢኖሩ በጸጋ ላይ ጸጋን፤ በበረከት ላይ በረከትን እንደሚታደሉ ከነቢዪት ሐና ታሪክ የምናገኘው ትምህርት ነው፡፡

በእርግጥ በሞት ወይም በዝሙት ምክንያት ከትዳር አጋሮቻችን ጋር የተለያየን ምእመናን ፈቃደ ሥጋችንን መቋቋም የማይቻለን ከኾነ በሥርዓተ ቍርባን በድጋሜ ጋብቻ መመሥረት እንደምንችል በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ተደንግጓል፡፡ እናም በሞት ለተለያዩ ጥንዶች ሁለተኛ ጋብቻ ባይከለከልም ሳያገቡ እንደ ነቢዪት ሐና ራሳቸውን ጠብቀው መኖር ለሚፈልጉ ግን አለማግባት ይቻላል፡፡ ራስን ጠብቆ መኖር በእግዚአብሔር ለተመረጡ ሰዎች እንጂ ለዅላችን አይቻለንምና፡፡ ‹‹… እያንዳንዱ እግዚአብሔር እንደ አደለው ጸጋ ይኑር፤ ግብሩ እንዲህ የኾነ አለና፡፡ ገብሩ ሌላ የኾነም አለና፡፡ ነገር ግን ያላገቡትንና አግብተው የፈቱትን እንደ እኔ ኾነው ቢኖሩ ይሻላቸዋል እላቸዋለሁ፡፡ በፍትወት ከመቃጠል ማግባት ይሻላልና …፤›› እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ /፩ኛ ቀሮ.፯፥፯-፱/፡፡

ነቢዪት ሐና በድንግልና ከመኖሯ እና ሁለተኛ ባል ካለማግባቷ ባሻገር ዓለማዊ ተድላና ደስታን ንቃ፣ ሰውነቷን ጠብቃ፣ ከምኵራብ ሳትወጣ ሰማንያ ዓመት ሙሉ እግዚአብሔርን ስታገለግል መኖሯ ከእርሷ የምንማረው ሌላኛው ቁም ነገር ነው፡፡ እኛም እንደ ነቢዪቷ ሙሉ ጊዜአችንን ለቤተ ክርስቲያን መስጠት ባይቻለን እንኳን ከሥጋዊው ሥራችን ጎን ለጎን ወደ ቤተ ክርስቲያን እየሔድን ትምህርተ ወንጌል ብንሰማ፣ ብንጸልይ፣ ብንሰግድ፣ ከምሥጢራት ብንሳተፍ፤ እንደዚሁም ለአቅማችን በሚመጥን ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ተልእኮ ብናገለግል የእግዚአብሔር ጸጋ በእኛ ላይ ይበዛል፤ እጥፍ ድርብም ይኾናል፡፡ ከዅሉም በላይ በምድራዊው ሕይወታችን የክርስቶስ ቤተ መቅደስ የኾነውን ሰውነታችንን ከኀጢአት ለይተን፣ ራሳችንን ለጽድቅ ሥራ አስገዝተን፣ በመንፈሳዊ ምግባር ጸንተን፣ ስንበድል ተጸጽተን (ንስሐ ገብተን)፣ ቅዱስ ሥጋውን በልተን፣ ክቡር ደሙን ጠጥተን ብንኖር የማያልፈውን መንግሥቱን ለመውረስ እንበቃለን፡፡

የጌታችን የመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ፣ የነቢዩ ስምዖን እና የነቢዪት ሐና፣ የሌሎችም ቅዱሳን በረከት ይደርብን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

‹‹በእኛ ቤተ ክርስቲያን ሰላም የዘወትር መልእክት ነው፡፡››  ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

 pat

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የካቲት ቀን ፳፻፱ .

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ከየካቲት ፩ – ፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በስዊዘርላንድ ጄኔቭ የአራት ቀናት ፓትርያርካዊ ጉብኝት አካሔዱ፡፡

በአራት ቀናት ቆይታቸውም በስዊዘርላንድ የሚገኘው የኦርቶዶክስ ማእከልን ጐብኝተዋል፤ ቦሲ በሚገኘው የሃይማኖት ተቋም ለሚማሩ ተማሪዎችና ሠራተኞች አባታዊ ምክር አስተላልፈዋል፤ ከዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ከፍተኛ አመራሮች ጋርም ተገናኝተዋል፡፡

ቅዱስ ፓትርያርኩ የካቲት ፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በጄኔቭ ከተማ በሚገኘው ዓለማቀፋዊ የሃይማኖት ጉባኤ ማእከል ቃለ ምዕዳን በሰጡበት ወቅት ከ፶ ሚሊዮን በላይ የሚኾኑ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንን በመወከል ለጉባኤው ሰላምታ ካቀረቡ በኋላ ዓለምን እርስበርስ የከፋፈለው ልዩነትን ከመቀነስ አኳያ ዓለም አቀፉ የአብያተ ክርስቲያናት ጉባኤ ያደረገውን ከፍተኛ ጥረት አድንቀዋል፡፡

የዓለም አቀፉ የአብያተ ክርስቲያናት ጉባኤ ሥራ ከመቼውም ጊዜ በላይ በዚህ ዘመን አስፈላጊ መኾኑን የገለጹት ቅዱስነታቸው ዛሬ በዓለም ዙሪያ የሚገኙ ክርስቲያኖች ለጥቃት፣ ለፈተና እና ለግጭት መጋለጣቸውን ጠቁመው የጉባኤው መርሖችና እና ዓላማዎች ከዚህ ቀደሙ በበለጠ መልኩ በአሁኑ ሰዓት በተግባር መተርጐም ይገባቸዋል ብለዋል፡፡

ecumenical

በስዊዘርላንድ ጄኔቭ ከተማ የሚገኘው ዓለማቀፋዊ የሃይማኖት ጉባኤ ማእከል

በተጨማሪም በዓለም ማኅበረሰብ መካከል ሰላምን ለማስፈን የሚሠራውን ዓለም አቀፉ የአብያተ ክርስቲያናት ጉባኤን እስካሁን ድረስ ለፈጸመው ስኬታማ ተግባር ምስጋናቸውን አቅርበው ጉባኤው ከተመሠረተበት ዓላማ አኳያ የሚጠበቁበት ቀሪ ሥራዎችን እንዲያከናውን የአደራ መልእክት አስተላለፈዋል፡፡

‹‹በእኛ ቤተ ክርስቲያን ሰላም የዘወትር መልእክት ነው›› ያሉት ቅዱስ ፓትርያርኩ የፍትሕ መጓደል፣ ጦርነት፣ ጠብ፣ ድህነት እና ጠባብ ብሔርተኝነት ዓለምን እርበርስ እንደ ከፋፈሏት ጠቅሰው ከእግዚአብሔር ቃል በስተቀር ሰብአዊ ፍልስፍናዎች፣ ከፍተኛ የምርምር ውጤቶች፣ ወይም የጦር መሣሪያዎች ሰላምን እና እርቅን ማስፈን እንደማይችሉ በቃለ ምዕዳናቸው አስታውቀዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ጉብኝታቸውን አጠናቀው የካቲት ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም  ወደ መንበረ ፓትርያርካቸው ወደ ኢትዮጵያ ተመልሰዋል፡፡

ምንጮች፡-

  • http://christiannewswire.com/news/7655779096.html
  • http://www.oikoumene.org/en/press-centre/news/patriarch-matthias-201cpeace-is-the-message-of-every-day201d

መንፈሳውያን በዓላት እና አሉታዊ አስተሳሰቦች – ካለፈው የቀጠለ

ketera1

በዳዊት አብርሃም

የካቲት ቀን ፳፻፱ .

ስለ በዓላት አሉታዊ አስተሳሰቦች

፩. በዓላት ድህነትን ያስፋፋሉ

በዓላት ድህነትን ያስፋፋሉ የሚሉ ወገኖች እንደ ምክንያት የሚያነሡት በበዓላት ሰዎች ከተግባረ ሥጋ ታቅበው ረፍት ስለሚያደርጉ የሥራ ሰዓት ይባክናል የሚል ነው፡፡ በተጨማሪም ለበዓላት የሚወጡ ወጪዎች ቍጠባ እንዳይኖር ያደርጋሉ በሚል መነሻ በዓላት ድህነትን ያባብሳሉ ብለው ይደመድማሉ፡፡ አስቀድመን እንደ ተመለከትነው በበዓላት ተግባረ ሥጋ ቢከለከልም መንፈሳዊ ሥራና በጎ አድራጎት አልተከለከለም፡፡ ተግባረ ሥጋም ቢኾን በዅሉም በዓላት በእኩል ደረጃ የተከለከለ አይደለም፡፡ መከልከሉም ደግሞ የሰው ልጅ ዕረፍት ስለሚያስፈልገው ነው፡፡ የሰው ልጅ ክቡር ፍጡር እንደ መኾኑ ዅልጊዜ እንደማሽን ሊሠራ ይገባዋል ማለት ሰብአዊ ክብርን የሚያንኳስስ አቋም ነው፡፡

ሠራተኛ ዕረፍት ማድረጉ ለበለጠ ሥራ ያነሳሣዋል እንጂ አያሰንፈውም፡፡ ዕረፍት ካደረጉ በኋላ የሠሩት ሥራ ደግሞ የበለጠ ጥራት ይኖረዋል፡፡ ሰው ዅልጊዜ ያለ ዕረፍት ሊሠራ ይገባዋል የሚሉ ወገኖች ሰዎችን እንደ ሰው ከመቍጠርና ከማክበር ይልቅ እንደ ቍስ የሚቈጥሩና ርኅራኄ የሌላቸው ናቸው፡፡ ሥራዎች የሚሠሩት በሰዎች ብቻ ሳይኾን ለሰዎችም ተብለው መኾኑ መዘንጋት የለበትም፡፡ ከባሪያ ፍንገላ ዘመን ጀምሮ በዘመናችን እስከሚገኘው ጭፍን የሀብት ማጋበስ ዘመን ድረስ ሰው ለጥቂት ባለ ሀብቶች የማይጠግብ ምኞት ቁቍስ አምራችና ገንዘብ ፈጣሪ እንዲኾን የሚያስገድደው ዓለማዊው ሥርዓት የሰውን ክብር የሚያሳውቀውን የክርስትና እምነት መቃወሙ አይገርምም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሰው መሥራት እንዳለበት ታስተምራለች፤ በዚያውም መጠን ዕረፍት እንደሚያስፈልገው ታምናለች፡፡

፪. መንፈሳውያን በዓላት ‹‹ካርኒቫል›› ናቸው

መንፈሳውያን በዓላት የሥጋዊ ደስታ መፍጠሪያ መንገዶች እንዲኾኑና ዓለማዊነት በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዲገባ የሚፈልጉ ወገኖች እንደ ጥምቀት ያሉ ክርስቲያንናዊ በዓላት በምዕራቡ ዓለም እንደሚታዩት ዓይነት በአብዛኛው ከባዕድ አምልኮ ጋር የተያያዘ የጀርባ ታሪክ እንዳላቸው በዓላት በስካርና ቅጥ ባጣ ፈንጠዝያ እንዲከበሩ ይፈልጋሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች የበዓላቱን መንፈሳዊነት አጥፍተው በዓላቱን ፍጹም ዓለማዊ በማድረግ በዓሉ ከሚያስገኘው ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ አንጻር ብቻ ሲመለከቱት ልብ ያላሉት ሌላ ነገር በዚህ መልኩ በዓላት መከበራቸው ሥርዓት አልባነትን እንደሚያነግሡና የሥነ ምግባር ውድቀት እንደሚፈጥሩ ነው፡፡ በዚህ መልክ የሚከበሩ በዓላት በምዕራቡ ዓለም ማኅበራዊ ቀውስን ሲፈጥሩ ይታያል፡፡ ከዅሉም በላይ ደግሞ በዓላቱ እውነተኛ ማንነታቸውን ካጡ የቱሪስት መስሕብ መኾናቸውም እንደሚቀር መታሰብ አለበት፡፡ የኢትዮጵያ ጥንታውያን በዓላት ‹‹ካርኒቫል›› ከኾኑማ አንድ ቱሪስት በዚያው በገዛ አገሩ እያለለት ለምን እኛ ዘንድ ይመጣል? ብሎ መጠየቅ ጉዳዩን በጥሞና ለማየት ይጠቅማል፡፡ (‹‹ካርኒቫል›› በዘፈን፣ በጭፈራ፣ ወዘተ በመሳሰሉ ዓለማዊ ባህሎች የሚከበር የአረማውያን በዓል ነው፡፡)

፫. በዓላት ዓለም አቀፍ ዕውቅና ማግኘታቸው መንፈሳዊነታቸውን ይቀንሰዋል

ዛሬ ላይ ያለችው ዘመናዊቷ ዓለም በምዕራባውያን ተጽዕኖ ሥር ያለች በመኾኗ ሳቢያ ምዕራባውያኑ የጐሰቈለ የሥነ ምግባር አቋማቸውን በዓለም አቀፍ ተቋማት በኩል እንዲሠራጭ ያደርጋሉ የሚል ስጋት ያላቸው ወገኖች ልክ የመስቀል በዓል እንደ ኾነው ዅሉ በዓላቱ ዩኔስኮን በመሰሉ ዓለም አቀፍ ተቋማት ዕውቅና ማግኘታቸውን በበጎ አያዩትም፡፡ የእኛም ቤተ ክርስቲያን እንደ ሌሎች ቤተ እምነቶች ወደ ዓለማዊነት ትንሸራተታለች ብለው ይፈራሉ፡፡ በእርግጥ ለቤተ ክርስቲያን ማሰብና ዓለማዊ ዝንባሌዎች ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዳይገቡ መጠንቀቅ ተገቢና አስፈላጊ ነገር ነው፡፡

ኾኖም ጠቃሚ ነገሮችን በይኾናል ስጋት ተሸብረን እንዳናስቀራቸው መጠንቀቅ ይኖርብናል፡፡ ዓለም አቀፍ ተቋማት ኢ ክርስቲያናዊ ሐሳቦችን መያዛቸው፣ እነዚህን ሐሳቦች እንደ ሕግ መቀበላቸውና ሀገራት እነዚህን እኩይ ሐሳቦቻቸውን ተቀብለው እንዲሠሩባቸው ጫና መፍጠራቸው ቤተ ክርስቲያን በዓለም አቀፍ ደረጃ ባለ መንቀሳቀሷ የተፈጠረ ክፍተት ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተጽዕኖዋን ለማሳረፍ ብትሠራ ዓለም እንደማያሸንፋት ጌታችን ቃል ገብቶላታል፡፡ ስለዚህ መንፈሳዊ በዓሎቻችን በዓለም አቀፍ ተቋማት ዕውቅና ማግኘታቸው በጎ እንጂ ክፉ አይደለም፡፡ ሥጋቶችን ወደ በጎ ዕድሎች የመቀየር አንዱ ዘዴ በመኾኑ ይህ ጥረት በሌሎች ዘርፎችም ሊቀጥል ይገባል፡፡

፬. በበዓላት የምእመናንን ሱታፌ የሚገድቡ አመለካከቶች

በቤተ ክርስቲያን ዅሉም አካላት ልዩ ልዩ ድርሻ አላቸው፡፡ ካህናቱና ሊቃውንቱ ብቻ አገልግለው ሌላው ምእመን ተመልካች አይኾንም፡፡ በበዓላትም ምእመናን በልዩ ልዩ መንገድ ያገለግላሉ፤ በዓሉን ያደምቃል፡፡ ለምሳሌ በበዓለ ጥምቀት ምእመናን ለየት ባሉ ግጥሞችና ዜማዎች እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ እንሰማለን፡፡ አንዳንድ ዘመን አመጣሽና ጥሩ ያልኾኑ ነገሮች በመጠኑ ቢታዩም በአብዛኛው የሕዝቡ ባህል ክርስቲያናዊ ነው፡፡ ዛሬ ዛሬ ታዳጊ ወንዶችና ልጃገረዶች በቡሄና ዘመን መለወጫ በዓላት የሚያዜሙት ዜማ ጠፍቶባቸው፣ ግራ ተጋብተው የምናየው ባህሉ በወጉ ለትውልድ መተላለፍ ባለመቻሉ ነው፡፡ ቀስ በቀስም ‹‹ነይ ነይ እምዬ ማርያም›› የሚለው የእናቶች ዜማ እየተዘነጋ እንዳይመጣ ያሰጋል፡፡ ስለኾነም ከዓለማዊ ዘፈን እና ከባዕድ ባህል ነጻ የኾኑ የሕዝብ የምስጋና ወይም የአገልግሎት ተሳትፎዎች ሊበረታቱ እንጂ ሊነቀፉ አይገባም፡፡

፭. በዓላትን በዓለማዊነት ፈለግ የማክበር ዝንባሌ

መንፈሳውያን በዓላት ከቤተ ክርስቲያን ያገኘናቸው፣ ታላላቅ መንፈሳዊ ትርጕሞችን ያዘሉ፣ ሰማያዊ ምሥጢራትን የያዙ፣ እኛን ከመለኮታዊ መገለጥ ጋር ድልድልይ ኾነው የሚያገናኙን ዕለታት ናቸው፡፡ እነዚህን በዓላት ከዓለም እንደ ተገኙ ዅሉ በዓለማዊ መርሐ ግብሮች ማክበር ከክርስቲያኖች አይጠበቅም፡፡ ከዚያም አልፎ አብዝቶ በመብላትና በመጠጣት፣ በመስከር ቅጥ ባጣ ፈንጠዝያ ማሳለፍ የበዓሉን ትርጕም ማዛባት ነው፡፡ በዓላት በሥርዓተ አምልኮ፣ በማኅሌት በቅዳሴ፣ በዝማሬ፣ በቃለ እግዚአብሔር፣ በክርስቲያናዊ ፍቅርና አንድነት፣ አብሮ በመብላት፣ ችግረኞችን በማስታወስ ሊከበሩ እንደሚገባው የቤተ ክርስቲያን የዘወትር ትምህርቷና ትእዛዟ ነው፡፡

፮. ክርስቲያናዊ በዓላትን ከባዕድ አምልኮ ጋር ማሻረክ

ክርስትና ጣዖትን ያጠፋ ሃይማኖት ነው፡፡ በጥንት ጊዜ በምዕራቡ ዓለም የጌታ ልደት በሚከበርበት ሰሞን ‹‹የፀሐይ ልደት›› እየተባለ የሚታሰብ የጦኦት አምልኮ ነበር፡፡ ሊቃውንቱ አማናዊው ፀሐይ ክርስቶስ ነውና በዚህ ዕለት የጌታችን ልደት እንዲከበር በማድረግ የሕዝቡን ልብ ከአምልኮ ጣዖት ወደ አምልኮ እግዚአብሔር መልሰውታል፡፡ በአገራችንም የመስቀል በዓል በሚከበርበት ሰሞን በደቡብ አካባቢ ይታሰብ የነበረውን ጣዖት አምልኮ ጻድቁ አቡነ ዜና ማርቆስ ካስወገዱ በኋላ በምትኩ የጌታችን መስቀል መገኘት መከበር መጀመሩ የሕዝቡን ልብ ከጣዖት አምልኮ እንዲርቅ አድርጎታል፡፡ የሰው መንፈስ ሲዝል ግን የጠፋው ባዕድ አምልኮ ያንሰራራል፡፡ ሰይጣንም ይህን ለማድረግ አይተኛም፡፡ የተሻሩ ጣዖታት አንዳንድ ጊዜ መንፈሳዊ በዓላት ላይ ጥላቸውን ያጠላሉ፡፡ በእመቤታችን ልደት ባዕድ አምልኮን የሚደብሉ፣ በሊቃነ መላእክት በዓላት ላይ በጠንቋይ ታዘው ዝክር የሚዘክሩ ሰዎች አሉ፡፡ እንደዚሁም በመስቀልና በጥምቀት በዓላት ላይ ለሰይጣን የሚሰዉ ዅሉ ቤተ ክርስቲያን የሰጠቻቸውን ክርስቲያናዊ በዓላት አርክሰዋልና በንስሐ ሊመለሱ፤ ለወደፊቱም ሊጠበቁ ይገባል፡፡

፯. የባዕድ በዓላትን ሳይመረምሩ መቀበል

በየጊዜው ከውጪ ሀገራት በተለይም ከምዕራባዊው ዓለም የሚገቡ በዓላት በዘመናችን ቍጥራቸው እየበዛ ነው፡፡ የእነዚህ ምዕራባዊ ባህሎች ተጽዕኖ ወደ ኢትዮጵያም በመዝለቅ ላይ ነው፡፡ ለአብነትም ‹‹ሀሎዊን›› በመባል የሚያታወቅ ከባዕድ አምልኮ ጋር የተቆራኘ፣ ክርስቲያኖች ሊያከብሩት የማይገባ የአሕዛብ በዓል በውጪ አገር በሚገኙ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች ከመከበር አልፎ በአገራችንም በአንዳንድ ቦታዎች መከበር መጀመሩ አሳሳቢ ነው፡፡ እንደዚሁም የጌታችንን ልደት በአገራችን የቀን አቈጣጠር ማክበር በቂ ኾኖ ሳለ ‹‹የፈረንጆች ገና›› እያሉ ማክበር ትክክል አይደለም፡፡

፰. የበዓል አከባበርን በባዕዳን ተጽዕኖ መቀየጥ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በዓላት በዋዜማ ይጀምራሉ፡፡ ማኅሌት ተቁሞ ስብሐተ እግዚአብሔር ይደርሳል፡፡ ካህናትና ምእመናን በሥርዓት ለብሰው በቤተ መቅደሱ በመገኘት እግዚአብሔርን እያመሰገኑ ያድራሉ፡፡ በበዓሉ ቀንም በየቤታቸው እየተገባበዙ ደስ ብሏቸው ይውላሉ፡፡ አሁን አሁን ግን የበዓሉን ዋዜማ በመሸታ ቤት፣ በዳንኪራና በስካር ማክበር እየተለመደ ስለመጣ ዋዜማን እኛጋ አክብሩ የሚሉ ጥሪዎች ከተለያዩ መዝናኛ ቦታዎች ይጎርፋሉ፡፡ ከዚህም ውጪ ‹‹የገና ዛፍ›› እንደሚባለው ያለ በእኛ ባህል ትርጕምም፣ ጥቅምም የሌለው እንዲያውም ባዕድ ከመኾኑም በላይ የተፈጥሮ ሀብትን የሚያወድምና አካባቢን የሚያራቁት ተግባር በመፈጸም ፈርጀ ብዙ ቀውስ ማድረሳችንን ማቆም አልቻልንም፡፡

፱. በዓላትን የሚያጥላሉ የመናፍቃን አስተሳሰቦች

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን እምነት፣ ሥርዓትና ትውፊት ማጥላላትና ማጠልሸት እንደ ዋና ሥራና ግብ አድርገው የሚሠሩ መናፍቃን በቤተ ክርስቲያን አጽዋማት ላይ ተቃውሞ እንደሚያነሡት ዅሉ በበዓላቶቿም ላይ የመረረ ተቃውሞን ይሰነዝራሉ፡፡ የመናፍቃኑ ተቃውሞ መጽሐፍ ቅዱስን በጭንብልነት የተጠቀመ ቢመስልም ምንም መጽሐፍ ቅዱሳዊ መረጃና መነሻ የሌለው ከመኾኑም በላይ እንዲያውም ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር የሚጣረስና በቤተ ክርስቲያን ታሪክ የምናውቀውን የቤተ ክርስቲያንን ትውፊት ያፋለሰ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ልጆች በመናፍቃኑ ሐሳብ እንዳይወሰዱ ወደ ቤተክርስቲያን ቀርበው ሊማሩ፤ ጥያቄዎችን ለመምህራን አቅርበው መልስ ሊያገኙ፤ ስለ በዓላት የተጻፉ መጻሕፍትንም ሊያነቡ ይገባል፡፡ ያ ካልኾነ ግን በዕውቀት ማጣት ምክንያት በመናፍቃን ወጥመድ መያዝና መሳት ይመጣል፡፡

፲. በዓላትን ለወቅታዊ ኹኔታዎች ማስገዛት

አንዳንድ ጊዜ በዓላት በሌሎች ውጫዊ አጀንዳዎች ሲጠመዱ ይታያል፡፡ ለወቅታዊ የአረማውያን ጥቃት ምላሽ ለመስጠት የሚያስችሉ ጽሑፎች የለጠፉ ልብሶችን (ቲ ሸርቶችን) በመልበስ፣ የዛቻና የማስፈራሪያ ይዘት ያላቸው ‹‹የካሴት›› መዝሙሮችን በማሰማት በዓላትን ማክበር አንዱ ችግር ነው፡፡ ሌላው ችግር መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልኾኑ ተቋማት፣ የፖለቲካ ቡድኖች፣ ወዘተ. የሚፈጥሩትን አጀንዳ ተሸክሞ በማሰብም ይኹን ባለማሰብ በመንፈሳዊ በዓላት ላይ ማቀንቀን፣ ‹‹ለመቻቻል›› እየተባለ ክርስቲያናዊ ያልኾኑ በዓላትን ማክበር ብዙ ጠንቅ አለው፡፡ ከኹሉም በላይ ደግሞ ሸቀጣቸው እንዲነሣላቸው የሚፈልጉ ነጋዴዎች የሚፈጥሯቸው በዓላትና የበዓላት አከባበሮች ክርስቲያኖችን የሸቀጥ ሰለባ እንዳያደርገን መጠንቀቅ አለብን፡፡ በአጠቃላይ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በዓላትን ስታከብር ሕግን ጠብቃና ሥርዓትን ሠርታ ስለኾነ ምእመናን በዓላትን በምናከብርበት ጊዜ ከኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ እንዳንወጣና ሥርዓቱንም እንዳናፋልስ መጠንቀቅ ይገባናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች!

ይህ ጽሑፍ በጥር ወር ፳፻፱ ዓ.ም በወጣው ፳፬ኛ ዓመት ቍጥር ፱ የሐመር መጽሔት ዕትም፣ ገጽ ፲፬ – ፲፯፤ ‹‹ቤተ ክርስቲያን የሰጠችንን በዓላት እንዴት እናክብራቸው?›› በሚል ርእስ ለንባብ መብቃቱን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡ 

መንፈሳውያን በዓላት እና አሉታዊ አስተሳሰቦች – ክፍል አንድ

ketera1

በዳዊት አብርሃም

የካቲት ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በዓል ‹‹አብዐለ-  አከበረ፤ አስከበረ›› ከሚለው ግስ የወጣ ሲኾን ትርጕሙም የደስታ፣ የዕረፍት ቀን፤ ያለፈ ነገር የሚታሰብበት፤ ሕዝብ የበዓሉን ምሥጢር እያሰበ ደስ ብሎት፣ ለብሶ፣ አጊጦ የሚዘምርበት፤ ዕልል የሚልበት ማለት ነው (ኪ.ወ.ክ. ገጽ ፪፸፰-፪፸፱)፡፡ ከዚህ መዝገበ ቃላዊ ፍቺ በርከት ያሉ ጽንሰ ሐሳባዊ ትርጕሞችን የምናገኝ ሲኾን የተወሰነቱን እንደሚከተለው እንመልከት፤

በዓላት የሚከበሩ ናቸው

በዓላት ምእመናን ከዘወትር ሥራዎቻቸው አርፈው በምትኩ መንፈሳዊ ተግባራትን በማከናወን የሚያከብሯቸው ናቸው፡፡ በቤተ ክርስቲያን ስለ በዓላት አከባበር በተሠራው ቀኖና በበዓላት ወቅት የማይፈጸም መንፈሳዊ ሥራ ስግደት ነው፡፡ ስግደት ሥጋን የሚያደክም ስለኾነ በበዓላት ወቅት አይሰገድም፡፡ ሌሎች መንፈሳዊ ሥራዎች ግን በበዓላት እንዲፈጸሙ ይፈቀዳል፡፡ ተግባረ ሥጋን በበዓላት መተው አስፈላጊ የሚኾንበት ምክንያት መንፈሳዊ ሥራ ለመሥራት እንዲቻል ነው፡፡

በዓላት የደስታ ዕለታት ናቸው

‹‹በዓል የሚያደርጉ ሰዎች የደስታና የምስጋና ቃል አሰሙ›› (መዝ.፵፩፥፭) እንደ ተባለው፤ በዓል የሚያዝኑበት፣ የሚያለቅሱበት፣ ከምግብ የሚከለከሉበት ወይም የሚጾሙበት ዕለት ሳይኾን ደስ የሚሰኙበት፣ በደስታ ውስጥም ኾነው እግዚአብሔርን የሚያመሰግኑበት ቀን ነው፡፡ ሐዋርያው ያዕቆብ ‹‹ደስ ያለው ይዘምር›› (ያዕ. ፭፥፲፬) እንዳለው የደስታ ቀን በኾነው በበዓል ስብሐተ እግዚአብሔር በስፋት ይቀርባል፡፡

በዓላት የዕረፍት ቀናት ናቸው

ሌሎች ቀናት የሥራ ቀናት ናቸው፡፡ በዓላት ግን ከእነዚህ ከብዙዎቹ ቀናት ተለይተው ሰው ከሥራው (ከተግባረ ሥጋው) የሚያርፍባቸው ዕለታት ናቸው፡፡ የበዓላት ጥንት የኾነችው ቀዳሚት ሰንበት እግዚአብሔር ሥነ ፍጥረትን ፈጥሮ ያረፈባት በመኾኑ እግዚአብሔር ሰዎች እንዲያርፉባት፤ በዕረፍትም ኾነው እንዲያከብሯት አዝዟል (ዘፍ. ፪፥፩-፫)፡፡ ኾኖም ማረፍ ማለት እጅና እግርን አጣጥፎ መዋል ማለት አይደለም፡፡ በዓላት ከተግባረ ሥጋ የሚታረፍባቸው ዕለታት ቢኾኑም በበዓላት ወቅት መንፈሳዊ ሥራ መሥራት ተገቢና አስፈላጊ መኾኑ ‹‹ክርስቲያኖች እንደ አይሁድ በዕለተ ቀዳሚት ሥራ ፈትተው መዋል አይገባቸውም፡፡ ይልቁንም ለክርስቲያን እንደሚገባ ሥራ ሊሠሩ ይገባቸዋል፤›› ተብሎ በፍትሐ ነገሥት ታዝዟል፡፡

በዓላት የመታሰቢያ ዕለታት ናቸው

እግዚአብሔር አምላክ አስቀድሞ ከሥራው ያረፈባትን የሰንበት ዕለት እንድናስባት አዝዞናል፡፡ ተአምራት ያደረገባቸውን፣ እስራኤል ዘሥጋን በግብጽ ባርነት ነጻ ያወጣበትንና የመሳሰሉትን ዅሉ በበዓላት እንዲታሰቡ አዝዟል (መዝ. ፻፲፥፬)፡፡ በሐዲስ ኪዳንም ‹‹ይህን ለመታሰቢያዬ አድርጉት›› በማለት አዝዟል (ሉቃ. ፳፪፥፱)፡፡ የፈጣሪን ሥራም ብቻ ሳይኾን ቅዱሳን ጻድቃንንና ሥራዎቻቸውን መዘከር የበዓላት አንዱ ገጽታ ነው፡፡ ‹‹የጻድቅ መታሰቢያ ለዘላለም ይኖራል›› ተብሎ መጻፉም ስለዚህ ነው (መዝ. ፻፲፯፥፳፬)፡፡

የበዓላት አከባበር

በዓላት በልዩ ልዩ መንገዶች ይከበራሉ፡፡ በበዓላት የሚከናወኑ መንፈሳዊና ሕዝባዊ ክንዋኔዎች አሉ፡፡ የተወሰኑ በዓላትን ሕዝብ ወደ ዐደባባይ በመውጣት በጋራ ያከብራቸዋል፡፡ አከባበሩም በዋናነት በጋራ ኾኖ የሚፈጸመውን ሥርዓተ አምልኮና የምስጋና ሥርዓት የሚያመለክት ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን እስራኤል ዘሥጋ በዓላትን ሊያከብሩ ወደ ዐደባባይ ሲወጡ ይዘምሩ ነበር፡፡ ይዘምሩዋቸው ከነበሩ ዝማሬያት መካከልም በመዝሙረ ዳዊት ከመዝሙር ፻፲፱ እስከ ፻፴፫ ያሉት የመዝሙር ክፍሎች ይገኙባዋል (የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ገጽ ፴፩)፡፡ ክቡር ዳዊትም በታቦቱ ፊት በቤተ መቅደስ ምስጋና የሚያቀርቡ ካህናትን መድቦ ነበር (፩ኛ ዜ.መ. ፲፮፥፬)፡፡

በአገራችን ኢትዮጵያ በዐደባባይ ከሚከበሩ በዓላት መካከል ቤተ ክርስቲያን የምታውቃቸው ሁለት ዋና ዋና በዓላት የሚገኙ ሲኾን እነዚህም በዓለ መስቀልና በዓለ ጥምቀት ናቸው፡፡ ከዐደባባይ በዓላት መካከል በዓለ መስቀል በዩኔስኮ ከማይዳሰሱ የዓለም ቅርሶች ተርታ ለመመዝገብ የበቃ ታላቅ በዓል ሲኾን ጥምቀትም በዐደባባይ በዓልነቱ ከአማንያኑ በተጨማሪ የብዙዎችን በተለይም የውጪ ቱሪስቶችን በመሳብ ተወዳዳሪ የሌለው ታላቅ በዓል ነው፡፡ ከወር በፊት በድምቀት ያከበርነው በዓለ ጥምቀት ቤተ ክርስቲያናችን ታቦታትን በማውጣት የምታከብረው ዐቢይ በዓል ነው፡፡ ጌታችን በመዋዕለ ሥጋዌው የሦስት ዓመት ከሦስት ወር የማስተማር ሥራውን የጀመረው በጥምቀት ነው፡፡ በየዓመቱ የጥምቀት በዓል የሚከበረውም ይህን ምሥጢር ለመዘከርና ለመመስከር ነው፡፡

ጌታችን ያሳየውን ትሕትና እና ለእኛ አርአያ መኾኑን ለመመስከር፣ ለጥምቀት ኀይልን ለመስጠት እንደዚሁም ውኃን ለመቀደስ ቤተ ክርስቲያን በዓለ ጥምቀቱን በየዓመቱ ታከብራለች፡፡ በየዓመቱ ውኃ ዳር ሔዶ ማክበር በየዓመቱ መጠመቅ ተብሎ እንዳይተረጐምና ሰዎችን እንዳያሳስትም ታስተምራለች፡፡ ይህንኑ ትምህርት ለማስገንዘብም ‹‹የጠበሉን መረጨት አይተው በቀድሞ ዘመን ወደ አገራችን መጥተው የነበሩ ኢየሱሳውያን፣ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ታጠምቃለች ብለው አጥላልተው ጽፈዋል፡፡ ነገር ግን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ይህን የምትፈጽመው ጌታችን ለኛ ብሎ ያሳየውን ትሕትና ለመመስከር፣ የጌታን በረከተ ጥምቀት ለምእመናን ለማሳተፍ እንጂ የተጠመቁትን ምእመናን እየደመለሰች በየዓመቱ አታጠምቅም፤›› ሲሉ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ ጽፈዋል (የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ታሪክ ገጽ ፻፳፫)፡፡

የጥምቀት በዓል አከባበር ሥርዓት ከሌሎቹ በዓላት የተለየ ነው፡፡ ታቦታቱ ከመንበረ ክብራቸው ወጥተው በበዓሉ ዋዜማ በሕዝብ ታጅበው ወደ ወንዝ ዳር ይወርዳሉ፡፡ በዚያ ዳስ ተጥሎ፣ ከተራም ተከትሮ ሌሊቱን መዘምራኑ በማኅሌት ካህናቱ በሰዓታት እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ ያድራሉ፡፡ ይህም ጌታ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ የመሔዱ ምሳሌ ነው፡፡ ሲነጋም ጸሎተ ቅዳሴው ተጠናቅቆ ወደ ወንዙ በመሔድ ጸሎተ አኮቴት ተደርሶ፣ ዐራቱ ወንጌላት ከተነበቡ በኋላ ውኃው ተባርኮ ለተሰበሰበው ሕዝብ ይረጫል፣ ወንዝም ሲሆን ሰዎች እየገቡ ሊጠመቁ ይችላሉ፡፡ በግብጽ ቤተ ክርስቲያንም፣ ከ6ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በፊት ዓባይ ወንዝ ወርደው በድምቀት ያከብሩት ነበር፡፡ ከዐረቦች መግባት በኋላ ግን ከሊፋዎቹ (ሡልጣኖቹ) ስለከለከሏቸው በቤተ ክርስቲያን ብቻ ለማክበር ተገድደዋል (The Coptic encyclopedia P.1103)፡፡

ከበዓለ መስቀል እና በዓለ ጥምቀት በተጨማሪ ‹‹አሸንዳ›› (‹‹አሸንድዬ››) በመባል የሚታወቀውና በሰሜን ኢትዮጵያ የሚከበረው የዐደባባይ በዓልም ሙሉ በሙሉ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የሚከናወን በዓል ባይኾንም ሕዝቡ በአለባበሱ፣ በአዘማመሩና በሚያደርጋቸው ሌሎች ክዋኔዎች በዓሉ እንደ ሌሎች ሕዝባዊ ባህሎች አረማዊ ወግን ያልተከተለ መኾኑን የሚያመለክቱ ናቸው፡፡

የበዓላት ፋይዳ

በዓላት በቀዳሚነት የሚከበሩት መንፈሳዊ ዓላማ ይዘው ነው፡፡ ኾኖም በዓላት በሕዝብ የሚከበሩ እንደ መኾናቸው ሌሎች ጥቅሞችም አሏቸው፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ ሰው መሥራት ብቻ ሳይኾን ማረፍም አለበትና በዓላት ለማረፍና ለመዝናናት ጠቀሜታ አላቸው፡፡ በዅሉም ሀገራት ያሉ ሃይማኖታዊ በዓላት ግብይትን በማሳለጥና የገንዘብ ዝውውርን በማፋጠን ለአገር ኢኮኖሚ ማደግ አስተዋጽኦ እንዳላቸው የመስኩ ባለሙያዎች ያስረዳሉ፡፡ ሌላው የበዓላት ጥቅም ደግሞ ማኅበራዊ ግንኙነትን ማዳበር ነው፡፡ በበዓላት ሰዎች ይገናኛሉ፤ ስጦታዎችን ይለዋወጣሉ፤ ይገባበዛሉ፡፡ በዚህም ማኅበራዊ ግንኙነታቸውን ያዳብራሉ፡፡ በበዓላት ወቅት ችግረኞች ርዳታ ያገኛሉ፡፡

ከዚህም በላይ በዓላት ለባህል ግንባታ ለመልካም ዕሴት መፈጠር ምክንያት ኾነው ሊያገለግሉ ይችላሉ፡፡ በዓላት የቱሪስት መስሕቦችም ናቸው፡፡ እንደ በዓለ መስቀል በዓለም አቀፍ ደረጃ ዕውቅና ያገኙ፣ እንደ ጥምቀት ብዙ ሕዝብን የሚያሳትፉ በዓላት የአገር ውስጥ ቱሪዝምን ከመፍጠራቸውም ባሻገር የውጪ አገር ሰዎች ብዙ ኪሎ ሜትሮችን አቋርጠው መጥተው እንዲጐበኙ ዕድል ይፈጥራሉ፡፡ በዚህም አገር የውጪ ምንዛሪ ታገኛለች፡፡ ከዅሉም በላይ በዓላት የአገርን ገጽታ ይገነባሉ፡፡ በተለይ ኢትዮጵያን በመሰለች ስሟ በድርቅና በረኀብ ለምትነሣ አገር በዓላት መጥፎ ገጽታንና ክፉ ስምን የሚቀይሩ ፍቱን መድኀኒቶች ናቸው፡፡

ስለ በዓላት አሉታዊ አስተሳሰቦች

የቤተ ክርስቲያን በዓላት የተጠቀሱትና ሌሎች ያልተጠቀሱ በርካታ ጥቅሞች እንዳሏቸው የታወቀ ቢኾንም አንዳንድ ወገኖች ግን በማወቅም ይኹን ባለማወቅ በዓላትን የሚዘልፉና የሚያንቋሽሹ ወይም የበዓላቱን ዓላማ የሚቃረኑ ሐሳቦችን ያዛምታሉ፡፡ በዚህ ጽሑፍ ከእነዚህ የተቃርኖ ሐሳቦች መካከል ጥቂቶቹን በመጥቀስና የሐሳቦቹን ድክመት በማሳየት ምላሽ እንሰጥባቸዋለን፤

ይቆየን

ክብረ በዓላት በመጽሐፍ ቅዱስ

timket

በዲያቆን ዘአማኑኤል አንተነህ

የካቲት ፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በዓል ማለት ‹‹አብዐለ – አከበረ›› ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጕሙም ‹‹መታሰቢያ ማድረግ፣ ማክበር›› ማለት ነው፡፡ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌም በመዝገበ ቃላታቸው ‹‹በዓል (ላት) በቁሙ፣ የደስታ፣ የዕረፍት ቀን፤ በዓመት፣ በወር፣ በሳምንት የሚከበር፤ ያለፈ ነገር የሚታሰብበት፤ ሕዝብ የበዓሉን ምሥጢር እያሰበ ደስ ብሎት እና ለብሶ፣ አጊጦ የሚዘፍንበት የሚዘምርበት፤ ዕልል የሚልበት፤ ሽብሸባ፣ ጭብጨባ የሚያደርግበት፤ ሲያረግድ እስክስታ ሲወርድ ባንገቱ የሚቀጭበት እንደ ጥጃ የሚፈነጭበት ነው›› በማለት የበዓልን ትርጕም ገልጸውታል፡፡ በአጠቃላይ በዓል ማለት ማሰብ፣ መዘከር፣ ማስታወስ የሚል ትርጕም አለው፡፡

የበዓላት ዑደት

እግዚአብሔር አምላካችን ‹‹ይህም ቀን መታሰቢያ ይኹናችሁ፤ ለእግዚአብሔርም በዓል ታደርጉታላችሁ፡፡ ለልጅ ልጃችሁ ሥርዓት ኾኖ ለዘለዓለም ታደርጉታላችሁ፤›› በማለት በዓል ዘለዓለማዊ መታሰቢያ እንደ ኾነ ተናግሯል /ዘፀ.፲፪፥፲፬-፲፯፤ ዘሌ.፳፫፥፪-፬/፡፡ ስለዚህም በዓላት በዓመታት፣ በወራት እና በሳምንታት ዑደት እየተመላለሱ ይከበራሉ፡፡ በየዓመቱ ከምናከብራቸው መንፈሳውያን በዓላት መካከል በዓለ ልደት፣ በዓለ ጥምቀት፣ በዓለ ትንሣኤ ይጠቀሳሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ የልደት በዓልን የምታከብረው ክርስቶስ በየዓመቱ የሚወለድ ኾኖ አይደለም፤ የልደቱን መታሰቢያ ለማሰብ ነው እንጂ፡፡ ጥምቀትን ስታከብርም የወንጌልን አስተምህሮ ተከትላ፣ ምሥጢር አስተካክላ፣ ወቅቱን ‹‹ዘመነ አስተርእዮ›› ብላ ሰይማ የክርስቶስን መገለጥ በማስተማር በዓሉን ታስበዋለች፡፡ የጥምቀት በዓልን እኛ ምእመናን ስናከብርም ዅልጊዜ እንጠመቃለን ማለት አይደለም፤ በዓሉን የምናከብረው ክርስቶስ መጠመቁን ለመዘከር፤ ከበረከቱም ለመሳተፍ ነው፡፡ በዓለ ትንሣኤን የምናከብረውም የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ በማሰብ፣ የእኛንም ትንሣኤ ተስፋ በማድረግ ነው እንጂ ጌታችን በየዓመቱ ከሙታን ይነሣል በማለት አይደለም፡፡ ሌሎችን በዓላትም እንደዚሁ፡፡

በዓላትን በማክበራችን ምን ጥቅም እናገኛለን?

፩. በረከት

‹‹አምላክህ እግዚአብሔር በፍሬህ ዅሉ በእጅህም ሥራ ዅሉ ይባርክሃልና እግዚአብሔር በመረጠው ስፍራ ለአምላክህ ለእግዚአብሔር ሰባት ቀን በዓል ታደርጋለህ፤ አንተም ፈጽሞ ደስ ይልሃል፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ /ዘዳ.፲፮፥፲፭/ በዓል ማክበር በረከትን ያሰጣል፡፡

፪. ፍጹም ደስታ

በዓል ስናከብር መንፈሳዊ ደስታ ይሰማናል፡፡ በበዓላት ወቅት እርስበርስ በመጠራራት ቤተሰብ ከሩቅም ከቅርብም ይሰባሰባል፤ ዕለቱ የደስታ ቀን ነውና፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ሙሴም ‹‹አንተም፣ ወንድ ልጅህና ሴት ልጅህ፣ ወንድ ባሪያህ እና ሴት ባሪያህ፣ በአገርህም ደጅ ውስጥ ያለ ሌዋዊ እና መጻተኛ፣ ድሃ አደግ እና መበለትም በበዓል ደስ ይበላችሁ፤›› በማለት በበዓል ቀን በዓሉን በማክበር መደሰት እንደሚገባ ይናገራል /ዘዳ.፲፮፥፲፬/፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊትም በመዝሙሩ ‹‹በዓል የሚያደርጉ ሰዎች የደስታ እና የምስጋና ቃል አሰሙ፤›› ይላል /መዝ.፵፪፥፬/፡፡ ነቢዩ ዕዝራ ደግሞ ‹‹እግዚአብሔር ደስ አሰኝቷቸዋልና የቂጣውን በዓል ሰባት ቀን በደስታ አደረጉ፤›› ሲል የእስራኤላውያንን በበዓል ቀን መደሰት አስረድቶናል /ዕዝ.፮፥፳፪፤ ፪ኛ ዜና መዋዕል ፴፥፳፫-፳፭/፡፡ በአገራችን አባባልም ‹‹አብሮ የበላን ቅዱስ ዮሐንስ አይሽረውም›› እንደሚባለው በዓመት በዓል ሕዝበ ክርስቲያኑ እርስበርስ እየተጠራራ አብሮ በመብላት በመጠጣት ይጫወታል፤ ይደሰታል፡፡

የበዓላት ክብር እኩል ነውን?

በዓላት በክብር ይለያያሉ፤ ለምሳሌ የእመቤታችን በዓል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየወሩ በ፳፩ ቀን ይከበራል፡፡ መስከረም ፳፩፣ ኅዳር ፳፩፣ እና ጥር ፳፩ ቀን ደግሞ የእመቤታችን ዐበይት በዓላት ናቸው፡፡ እንደዚሁም የቅዱስ ሚካኤል በዓል ወር በገባ በ፲፪ኛው ቀን ይከበራል፡፡ ኾኖም ግን የቅዱስ ሚካኤል ዐቢይ በዓል የሚከበረው በየዓመቱ በኅዳር ፲፪ እና ሰኔ ፲፪ ቀን ነው፡፡ የቅዱስ ገብርኤል ደግሞ በየወሩ በ፲፱ ቀን በዓሉ ቢታሰብም ታኅሣሥ እና ሐምሌ ፲፱ ቀን ዐቢይ በዓሉ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በወር ውስጥ የሚገኙትን እያንዳንዱን ቀናት በቅዱሳን ስም ብትሰይምም በዓላትን በዐቢይነትና ታቦታትን በማውጣት የምታከብራቸው በዓመት አንድ ወይም ሁለት ጊዜ ነው፡፡ ከዚህ ሥርዓትም በዓላት በአከባር የተለያዩ መኾቸውንና ልዩ የበዓል ቀኖችም እንዳሉ እንረዳለን፡፡ በመጽሐፈ ዜና መዋዕል ካልዕ ምዕራፍ ፴፥፳፮ ላይ ‹‹በኢየሩሳሌም ታላቅ ደስታ ኾነ፤ ከእስራኤል ንጉሥ ከዳዊት ልጅ ከሰሎሞን ዘመን ጀምሮ እንደዚህ ያለ በዓል በኢየሩሳሌም አልተደረገም ነበር፤›› ተብሎ የተጻፈው ኃይለ ቃል ለዚህ ማረጋገጫችን ነው፡፡

በዓላትን አለማክበር ምንን ያመጣል?

፩. ረድኤተ እግዚአብሔርን ያርቃል

በሰቆቃወ ኤርምያስ ምዕራፍ ፩፥፬ ላይ ‹‹ዳሌጥ፣ ወደ ዓመት በዓልም የሚመጣ የለምና የጽዮን መንገዶች አለቀሱ፡፡ በሮችዋ ዅሉ ፈርሰዋል፡፡ ካህናቶችዋም እየጮኹ ያለቅሳሉ፤ ደናግሎችዋም ተጨነቁ፡፡ እርስዋም በምሬት አለች፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ በዓላትን በማክበራችን ከእግዚአብሔር በረከትን እንደምንቀበል ዅሉ ባለማክበራችን ደግሞ ረድኤተ እግዚአብሔር ከእኛ ይርቃል፡፡

፪. ቅጣትን ያስከትላል

በመጽሐፈ ሳሙኤል ካልዕ እንደ ተገለጸው የእግዚአብሔር ታቦት ወደ ዳዊት ከተማ በገባ ጊዜ ነቢዩ ዳዊት በደስታ ምስጋና ያቀርብ ነበር፡፡ ሚስቱ ሜልኮል ግን ሲዘምር ባየችው ጊዜ ንጉሥ ኾኖ ሳለ ራሱን አዋረደ በሚል ሐሳብ ባለቤቷ ንጉሥ ዳዊትን ናቀችው፡፡ ዳዊትም ሜልኮልን ‹‹በእግዚአብሔር ፊት ዘፍኛለሁ፤ በእግዚአብሔር ሕዝብ በእስራኤል ላይ አለቃ እኾን ዘንድ ከአባትሽ እና ከቤቱ ዅሉ ይልቅ የመረጠኝ እግዚአብሔር የተባረከ ይኹን፡፡ ስለዚህም በእግዚአብሔር ፊት እዘምራለሁ፤›› በማለት ለእግዚአብሔር ምስጋና ማቅረብ እንደሚያስከብርና ከፍ ከፍ እንደሚደርግ ተናግሯል፡፡ እግዚአብሔርም ለአምላኩ የዘመረውን ዳዊትን በመናቋ ልጅ እንዳትወልድ የሜልኮልን ማኅፀን ዘግቶታል /፪ኛ ሳሙ. ፮፥፲፮-፳፫/፡፡ ከዚህ ታሪክ በዓሉን ብቻ ሳይኾን በዓሉን የሚያከብሩ ሰዎችንም ማክበር እንደሚገባን እንማራለን፡፡ ‹‹ዕልልታን የሚያውቅ ሕዝብ ምስጉን ነው፤›› እንዳለ ቅዱስ ዳዊት /መዝ.፹፱፥፲፭/፡፡

በክብረ በዓላት ምን ዓይነት ልብስ መልበስ አለብን?

ሰው ወደ ሰርግ ሲጠራ ከቤቱ ያለውን፣ የተሻለውን ልብስ መርጦ እንዲለብስ መንፈሳውያን በዓላት የቤተ ክርስቲያን የክብሯ መግለጫ ቀናት እንደ መኾናቸው መጠን እኛ ክርስቲያኖችም በእነዚህ ቀናት የምንለብሰው ልብስ የተለየ መኾን ይገባዋል፡፡ የሌሊት ልብስ ለብሶ ወደ ቤተ ክርስቲያን መሔድ እንደማይገባ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ተደንግጓል፡፡ በገዳማውያን አባቶች ዘንድ ለቅዱስ ቍርባን መቀበያ የሚኾን ልብስ ከሌሎች አልባሳት ተለይቶ ውኀ፣ ጭስ፣ አቧራ ከማይደርስበት ቦታ ይቀመጣል፡፡ አባቶች ይህንን ልብስ የሚለብሱት ለቅዱስ ቍርባን ብቻ ነው፡፡ በገጠሩ የአገራችን ክፍልም ልጆች ልብስ የሚገዛላቸው በአብዛኛው በጥምቀት ወቅት ነው፡፡ ይህም ለበዓሉ የሚሰጠውን ልዩ ክብር ያስረዳናል፡፡ እናቶቻችንም ‹‹ለጥምቀት ያልኾነ ቀሚስ ይበጣጠስ›› እያሉ በበዓለ ጥምቀት ያላቸውን አዲስ ቀሚስ አውጥተው ይለብሳሉ፡፡

በዓመት በዓል ቀን እንስሳት የሚታረዱት ለምንድን ነው?

በዓል ሲደርስ ገበያው ይደምቃል፤ ቤታችን ያምርበታል፡፡ እንበላቸው ዘንድ የተፈቀዱ እንስሳት ይታረዳሉ፡፡ በተለይም በገጠሩ የሀገራችን ክፍል ለፋሲካ፣ ለልደት እየተባለ በግ ተቀጥቅጦ  ይቀመጥና ጊዜው ሲደርስ ይታረዳል፡፡ በበዓላት ቀን የከብት፣ የበግ፣ የፍየል መሥዋዕት ይቀርብ እንደ ነበር መጽሐፍ ቅዱስ ያስረዳል፡፡ መጽሐፈ ዕዝራ ፫፥፬ ‹‹እንደ ተጻፈውም የዳስ በዓል አደረጉ፤ እንደ ሥርዓቱም ለዕለቱ የተገባውን የየዕለቱን የሚቃጠል መሥዋዕት በቍጥር አቀረቡ፤›› ይላል፡፡ ዛሬም በበዓላት ቀን በየቤተ ክርስቲያኑ እና በየቤቱ የሚታረደው ይህንኑ አብነት በማድረግ ነው፡፡ (በተጨማሪም ዘሌ.፳፫፥፴፯፤ ሕዝ.፵፮፥፲፩ ይመልከቱ)፡፡

በአጠቃላይ በዓላትን ከሥጋዊ ሥራ ተከልክሎ ማክበር እንደሚገባ ቅዱሳት መጻሕፍት ይናገራሉ፡፡ ‹‹በመጀመሪያው ቀን የተቀደሰ ጉባኤ ይኹንላችሁ፤ የተግባር ሥራ ዅሉ አትሥሩበት፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ /ዘሌ.፳፫፥፯/፡፡ የበዓላት አከባበርም እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውኃ ፈሳሽ በኾነ ባህል ሳይኾን ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን በጠበቀ፤ የበዓሉን መንፈሳዊ ታሪክ በተመረኮዘ መንገድ የተሰጠን ትእዛዝ ነው፡፡ ዮሴፍ ወልደ ኮሪዮን በዜና አይሁድ መጽሐፉ እንደ ጠቀሰው አይሁድ በዕለተ ሰንበት ወደ መጸዳጃ ቤት እንኳን አይሔዱም ነበር፡፡ እኛ ግን እንደ አይሁዳውያን በተጋነነ መንገድ ሳይኾን ሰውነትን ከሚያደክም ሥጋዊ ሥራ ተከልክለን በዓላትን እንድናከብር በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ተደንግጓል፡፡

አገራችን ኢትዮጵያ አስቀድማ በሕገ ልቦና እግዚአብሔርን ስታመልክ የኖረች በኋላም መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕፀ መስቀሉ የቀደሳት፣ በኪደተ እግሩ የባረካት አገር ናት፡፡ ኢትዮጵያውያን ምእመናን ከጥንት ጊዜ ጀምሮ መጽሐፍ ቅዱስን መሠረት አድርገው መንፈሳውያን በዓላትን በሥርዓት ሲያከብሩ ኖረዋል፡፡ አሁን አሁን ግን በብዙዎቻችን ዘንድ እንደሚስተዋለው የበዓላት አከባበር ሥርዓት እየተጣሰ ይገኛል፡፡ በበዓላት ቀን ሥራ መሥራት እየተለመደ መጥቷል፡፡ ይህ ልማድ ሊስተካከልና ሊቀረፍ ይገባል፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም እንደ በዓለ ጥምቀት ባሉ የዐደባባይ በዓላት ወቅት የሚታየው የሥጋዊ ገበያ ግርግር ክርስቲያናዊ የበዓላት አከባበር ሥርዓትን እንዳያጠፋብን ልንጠነቀቅ ያስፈልጋል፡፡

በአገራችን ብሂል ‹‹በዓል ሽሮ የከበረ፣ ጦም ገድፎ የወፈረ የለም›› እንደሚባለው በዓላትን መሻር ከሚሰጠው ትርፍ ይልቅ የሚያመጣው መቅሠፍት ይብሳልና በዓላትን ለሥጋዊ ጉዳይ መጠቀሚያ ከማድረግ ይልቅ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን መሠረት አድርገን በአግባቡ ማክበር ይገባናል፡፡ አንድ ክርስቲያን መንፈሳውያን በዓላትን በሥርዓት ሲያከብር የሚመለከቱ አካላት ‹‹ሃይማኖቱ እንዴት ደስ ይላል? እኛም እንደ እርሱ በኾንን›› በማለት እርሱንም ሃይማኖቱንም ያደንቃሉ፤ መንፈሳዊ ቅናትንም ይቀናሉ፡፡ ስለዚህም የጥንቱን ሥርዓት ጠንቅቀን፣ መልኩን ሳንለውጥ፣ ሥርዓቱንም ሳናፋልስ በዓላትን ማክበር ይገባናል፡፡ በዓላትን በሥርዓቱ አክብረን በረከትን እናገኝባቸው ዘንድ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ነቢዩ ዮናስ ክፍል ሁለት

በልደት አስፋው

የካቲት ፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም  

እንዴት ናችሁ ልጆች? እኛ እግዚአብሔር ይመስገን በጣም ደኅና ነን፡፡ በትናንትናው ዝግጅታችን እግዚአብሔር አምላካችን ነቢዩ ዮናስን አስተምር ብሎ ወደ ነነዌ ሰዎች እንደ ላከው፣ እርሱ ግን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ላለመቀበል በመርከብ ተሳፍሮ ወደ ሌላ አገር እንደ ሸሸ፣ በነቢዩ ዮናስ ምክንያትም መርከቡ እስኪሰጥም ድረስ ባሕሩ በማዕበል እንደ ተናወጠ፣ በዚህ የተነሣም ተሳፋሪዎቹ ዕጣ ተጣጥለው ነቢዩ ዮናስን ወደ ባሕሩ እንደ ጣሉት ነግረናችሁ ነበር፡፡ ልጆች! ቀጣዩን ክፍል ደግሞ እንደሚከተለው አቅርበንላችኋል፤

እናም ሰዎቹ ነቢዩ ዮናስን ወደ ባሕር ሲጥሉት እግዚአብሔር ያዘጋጀው ታላቅ ዓሣ ዋጠው፡፡ ነቢዩ ዮናስም በዓሣው ሆድ ውስጥ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት ቆየ፡፡ በዚያ ጨለማ በኾነ የዓሣ ሆድ ውስጥ ለሦስት ቀን መቆየት አያስፈራም ልጆች? በጣም ነው የሚያስፈራው፡፡ ነቢዩ ዮናስም እግዚአብሔር እንዲያወጣው በዓሣው ሆድ ውስጥ ኾኖ አብዝቶ ጸለየ፡፡ እግዚአብሔርም የነቢዩ ዮናስን ጸሎት ሰምቶ ዓሣውን እንዲተፋው አዘዘው፡፡ ዓሣውም ነቢዩ ዮናስን በየብስ (በደረቅ መሬት) ላይ ተፋው፡፡ ነቢዩ ዮናስም ‹‹ይህቺ አገር ማን ትባላለች?›› ብሎ የአካባቢው ነዋሪዎችን ሲጠይቅ አገሪቱ ነነዌ እንደ ኾነች ነገሩት፡፡ ይገርማችኋል ልጆች! ከዚህ በኋላ ነቢዩ ዮናስ የእግዚአብሔርን ቃል እሺ ብሎ ተቀብሎ ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ገብቶ ‹‹በሦስት ቀን ውስጥ ነነዌ ትገለባበጣለች (ትጠፋለች)›› ብሎ አስተማረ፡፡

የነነዌ ሰዎችም ቃሉን ሰምተው ከኀጢአታቸው ተመልሰው፣ ማቅ ለብሰው ንስሐ ገቡ፡፡ ከከንጉሡ ጀምሮ ሕፃናትም ጭምር፣ እንስሳትም ሳይቀሩ ምንም ምግብ ሳይቀምሱ፣ ውኀም ሳይጠጡ ለሦስት ቀን ጾሙ፡፡ እንዲምራቸውም ወደ እግዚአብሔር ጮኹ፡፡ እግዚአብሔርም ከክፉ መንገዳቸው መመለሳቸውንና ንስሐ መግባታቸውን አይቶ ይቅር አላቸው፤ ነነዌንም ከጥፋት አዳናት፡፡ ልጆች ነቢዩ ዮናስ እግዚአብሔርን አልታዘዝም ያለው ለምን መሰላችሁ? እኔ ነነዌ ትገለባበጣለች (ትጠፋለች) ብዬ ባስተምር ሕዝቡ ተጸጽቶ ይቅርታ ቢጠይቁ እግዚአብሔር ይቅር ሲላቸው እኔ ውሸታም ነቢይ እባላለሁ ብሎ ፈርቶ ነበር፡፡ ነገር ግን የነነዌ ሰዎች ነቢዩ ዮናስንም ውሸታም ነው አላሉትም፡፡ ትምህርቱን ተቀብለው ከጥፋት በመዳናቸው እግዚአብሔርን አመስግነዋል፡፡ እግዚአብሔር ምን ያህል ሩኅሩኅና ቸር እንደኾነ አያችሁ ልጆች? ምንም እንኳን እኛ ብንበድለውም፣ ብናሳዝነውም ተጸጽተን ንስሐ ከገባን የቀደመውን በደላችንን ደምስሶ ኀጢአታቻንን ይቅር ይለናል፡፡

ልጆች ነነዌ ከመቶ ሃያ ሺሕ የሚበልጡ ሰዎችና ብዙ እንስሳት የሚኖሩባት ታላቅ ከተማ ነበረች፡፡ እነኚህ ዅሉ ሰዎች ንስሐ ባይገቡ ኖሮ ነነዌን እሳት ይበላት ነበር፡፡ የነነዌ ሰዎች ከበደላቸው ተጸጽተው፣ ንስሐ ገብተው በመጾማቸውና በመጸለያቸው እግዚአብሔር ከጥፋት አድኗቸዋል፡፡ ልጆች! እኛም ዛሬ እግዚአብሔርን ብንበድለውና እርሱ የማይወደውን ክፋት ብንፈጽም እንደ ነነዌ ሰዎች ተጽጽተን ንስሐ ከገባን አምላካችን ቸር፣ ታጋሽ እና ይቅር ባይ አምላክ ስለኾነ ኀጢአታችንን ይቅር ብሎ ከጥፋት ያድነናል፡፡ እኛ ክርስቲያኖች በየዓመቱ ጾመ ነነዌን የምንጾመውም እግዚአብሔር ኀጢአታቻንን ይቅር እንዲለን ነው፡፡ በሉ እንግዲህ ልጆች በሌላ ጊዜ በሌላ ታሪክ እስከምንገናኝ በደኅና ቆዩ፡፡ ሰላመ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይኹን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ነቢዩ ዮናስ ክፍል አንድ

እንደምን አላችሁ ልጆች? ከአሁን በፊት ለእናንተ የሚኾኑ ትምህርታዊ ጽሑፎችን በድረ ገጻችን ስናቀርብላችሁ ነበር፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን በልዩ ልዩ ምክንያት ዝግጅቱን አቋርጠን ቆይተናል፡፡ ለዚህም እናንተን ይቅርታ እየጠቅን ከዛሬ ጀምሮ ወቅታዊ ይዘት ያሏቸውን ትምህርታዊ ጽሑፎች በየጊዜው እንደምናቀርብላችሁ ቃል እንገባለን፡፡ በዛሬው ዝግጅታችንም የነቢዩ ዮናስንና የነነዌ ሰዎችን ታሪክ ይዘንላችሁ ቀርበናል፤ መልካም የንባብ ጊዜ ይኹንላችሁ!

ነቢዩ ዮናስ ክፍል አንድ

በልደት አስፋው

የካቲት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ልጆች! እግዚአብሔር ለሕዝቡ መልእክት ለማስተላለፍ ሲፈልግ ወደ ሕዝቡ ከሚልካቸው ነቢያት መከካል አንዱ ነቢዩ ዮናስ ነው፡፡ ታዲያ አንድ ቀን ምን ኾነ መሰላችሁ ልጆች፣ ወደ አንዲት ታላቅ ከተማ ሔዶ እንዲሰብክ የእግዚአብሔር ቃል ለነቢዩ ዮናስ መጣለት፡፡ ልጆች ይህች ታላቅ ከተማ ነነዌ ትባላለች፡፡ በዚህች በነነዌ ከተማ የሚኖሩ ሰዎች ኀጢአታቸው እጅግ በዝቶ ነበር፡፡ ርኅሩኁ አምላካችን እግዚአብሔር የሰውን መዳን እንጂ ጥፋቱን ስለማይፈልግ ንስሐ ግቡ ብሎ እንዲያስተምራቸው ነቢዩ ዮናስን ወደ ነነዌ ላከው፡፡ ነቢዩ ዮናስ ግን የፈጣሪውን ትእዛዝ ላለመፈጸም ሊኮበልል አሰበ፡፡ ከዚያም ተርሴስ ወደምትባል አገር የምታልፍ መርከብ አግኝቶ በእርሷ ተሳፈረ፡፡ ልጆች ከእግዚአብሔር ፊት መኮብለል ወይም መሸሽ ይቻላል? አይቻልም አይደል? እስቲ ነቢዩ ዮናስ የተሳፈረባት መርከብ ምን እንደ ገጠማት እንመልከት፤

ነቢዩ ዮናስ በመርከብ ተሳፍሮ ሲሔድም እግዚአብሔር ታላቅ ነፋስን አምጥቶ በባሕሩ ላይ ታላቅ ማዕበልን አስነሣ፡፡ በዚህ ጊዜ መርከቢቱ ልትሰበር ደረሰች፡፡ ለምን እንደዚህ እንደኾነ አወቃችሁ ልጆች? ነቢዩ ዮናስ ከእግዚአብሔር ፊት ለመሸሽ በማሰቡ ነው፡፡ መርከቢቷ ውስጥ ያሉ ሰዎችም እጅግ ፈሩ፡፡ መርከቧ ክብደት ስለበዛባት ነው ብለው አስበው በውስጧ የነበረውን ዕቃ ዅሉ ወደ ባሕር ቢጥሉትም መርከቢቱ ግን ልትረጋጋ አልቻለችም ነበር፡፡ ማዕበሉም አልቆም አለ፡፡ ልጆች ይህ ዅሉ ሲኾን ግን ነቢዩ ዮናስ ተኝቶ ነበር፡፡ ከዚያም የመርከቡ አለቃ ወደ እርሱ ቀረበና ‹‹ምነው ተኝተሃል? እንዳንጠፋ እግዚአብሔር ያስበን እንደኾነ ተነሥተህ አምላክህን ጥራ›› አለው፡፡ በመርከቡ ውስጥ ያሉት ሰዎችም ‹‹ይህ ክፉ ነገር በማን ምክንያት እንዳገኘን እናውቅ ዘንድ ኑ ዕጣ እንጣጣል›› ተባብለው ዕጣ ሲጣጣሉ ዕጣው በነቢዩ ዮናስ ላይ ወጣ፡፡ ሰዎቹም ነቢዩ ዮናስን ‹‹ይህ ክፉ ነገር በማን ምክንያት እንዳገኘን እባክህ ንገረን?›› አሉት፡፡

ነቢዩ ዮናስም ከእግዚአብሔር ፊት መኮብለሉን በነገራቸው ጊዜ ሰዎቹ በፍርኀት ኾነው ‹‹ይህ ያደረግኸው ምንድን ነው?›› አሉት፡፡ ባሕሩንም ሞገዱ እጅግ ያናውጠው ነበርና ‹‹ባሕሩ ጸጥ እንዲል ምን እናድርግብህ?›› ሲሉ ጠየቁት፡፡ እርሱም ‹‹ይህ ታላቅ ማዕበል በእኔ ምክንያት እንዳገኛችሁ አውቃለሁ፡፡ አንሥታችሁ ወደ ባሕር ጣሉኝ፡፡ ባሕሩም ጸጥ ይልላችኋል፤›› አላቸው (ትንቢተ ዮናስ ፩፥፩-፲፫)፡፡ ሰዎቹም ነቢዩ ዮናስን ወደ ባሕሩ ጣሉት፡፡ በዚህ ጊዜ ባሕሩ ከመናወጥ ጸጥ አለ፡፡ ልጆች! ባሕሩ ሲናወጥ የነበረው ለምን እንደኾነ ተረዳችሁ? ዮናስ እግዚአብሔር ያዘዘውን ትቶ ለመሸሽ በመርከቡ በመሳፈሩ ነው! እግዚአብሔርን ሳንታዘዝ ያሰብንበት ቦታ መድረስ የምንችል ይመስላችኋል ልጆች? አንችልም አይደል? አዎ፤ አንችልም፡፡ ምክንያቱም ዓለሙን ዅሉ የፈጠረ እግዚአብሔር ነውና በባሕርም ኾነ በየብስ (በደረቅ መሬት) ብንጓዝ ከእርሱ መሰወር ፈጽሞ አይቻለንም፡፡ እግዚአብሔር የሌለበት ቦታና ከእርሱ እይታ የተሰወረ ምንም ነገር የለምና፡፡

ልጆች! ቀጣዩን ክፍል ነገ ይዘንላችሁ እንቀርባለን እሺ? ለዛሬው ከዚህ ላይ ይቆየን፡፡

ጾመ ሰብአ ነነዌ

በርእሰ ደብር ብርሃኑ አካል

ጥር ፳፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጾመ ነነዌ ከሰባቱ የአዋጅ አጽዋማት አንዷ ስትኾን የምትጾመውም ለሦስት ቀናት ነው፡፡ ይህቺ ጾም የምትጀመርበት ዕለትም ልክ እንደ ዐቢይ ጾም ሰኞን አይለቅም፡፡ ጾሟ የምትጀመርበት ቀን ሲወርድ ወይም ወደ ኋላ ሲመጣ እስከ ጥር ፲፯ ቀን ድረስ ነው፡፡ ቀኑ ሲወጣ ወይም ወደ ፊት ሲገፋ ደግሞ እስከ የካቲት ፳፩ ቀን ይረዝማል፡፡ ጾመ ነነዌ በእነዚህ ፴፭ ቀናት ውስጥ ስትመላለስ (ከፍ እና ዝቅ ስትል) ትኖራለች፤ ከተጠቀሱት ዕለታት አትወርድም፤ አትወጣም፡፡ በዚህ ዓመትም (፳፻፱ ዓ.ም) ጥር ፳፱ ቀን ትጀመራለች፡፡

‹‹ጾመ ሰብአ ነነዌ፤ የነነዌ ሰዎች ጾም›› የሚለው የጽሑፋችን ርእስ እንደሚያስረዳው ይህቺን የሦስት ቀን ጾም የጾሟት በነነዌ ይኖሩ የነበሩ ሰዎች ናቸው፡፡ ከተማዋም (ነነዌ) በጤግሮስ ወንዝ ዳርቻ የምትገኝ ስትኾን መሥራቿም ናምሩድ ነው /ዘፍ.፲፥፲፩-፲፪/፡፡ ጥንታዊቷ የነነዌ ከተማ ለአሦር መነሻ የኾነች፤ እጅግ ሰፊና ያማረች፤ የቅጥሯ ርዝመትም ፲፪ ኪሎ ሜትር የሚሸፈን ነበር፡፡ በከተማዋ ንጉሡ ሰናክሬም ብዙ ሕንጻዎችን ገንብቶባት ነበር /ዮናስ ፬፥፲፩/፡፡ በዚያ ዘመን የነበሩ የነነዌ ሰዎች ኀጢአታቸው በዝቶ እግዚአብሔር ሊያጠፋቸው ሲል ቸርነትና ምሕረቱ የማያልቅበት እግዚአብሔር መክሮ፣ ዘክሮ እንዲመልሳቸውና ንስሐ እንዲገቡ ነቢዩ ዮናስን ወደ ነነዌ ሕዝብ ላከው /ሉቃ.፲፩፥፴/፡፡

ዮናስ የስሙ ትርጕም ‹ርግብ› ማለት ነው፡፡ በዳግማዊ ኢዮርብዓም ዘመነ መንግሥት የነበረ ነቢይ ነው፡፡ ይህ ነቢይ መኖሪያው በገሊላ በጋትሔፌር ድንበር ከተማ ነበረ፡፡ አባቱም አማቴ ይባላል፡፡ ኢዮርብዓም ሶርያውያንን አባሮ የእስራኤልን ድንበር እንዲመልስ ነቢዩ ዮናስ ትንቢትን ተናግሯል /፪ኛነገ.፲፬፥፳፭፤ ዮናስ ፩፥፩/፡፡ ነቢዩ ኤልያስ ያስነሣው የሰራጵታዋ መበለት ሕፃን ነቢዩ ዮናስ እንደ ኾነ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ያስረዳል /፩ኛነገ.፲፯፥፲፱/፡፡ መድኀኒታችን ክርስቶስም የዮናስን ከዓሣ ኾድ መውጣት የራሱ ትንሣኤ ምሳሌ አድርጎ ነግሮናል /ማቴ.፲፪፥፲፱-፵፪፤ ሉቃ.፲፩፥፴-፴፪/፡፡

እግዚአብሔር ‹‹ሔደህ በነነዌ ላይ ስበክ›› ባለው ጊዜ ነቢዩ ዮናስ ‹‹አንተ መሐሪ ነህ፤ ልትጠፉ ነው ብዬ ተናግሬ ብትምራቸው ሐሰተኛ ነቢይ እባላለሁ›› ብሎ ላለመታዘዝ እስራኤልን ለቆ በመርከብ ወደ ተርሴስ ሸሸ፡፡ እግዚአብሔርም ታላቅ ነፋስን አስነሥቶ መርከቧ በማዕበል እንድትመታ አደረገ፡፡ ከዮናስ ጋር በመርከቧ ተሳፍረው የነበሩ ነጋድያንም ያላቸውን ሀብት ወደ ባሕሩ መጣል ሲጀምሩ ነቢዩ ዮናስ ጥፋቱን ተገንዝቦ ‹‹ማዕበሉ በእኔ ምክንያት የመጣ ስለ ኾነ ንብረታችሁን ሳይኾን እኔን ወደ ባሕር ጣሉኝ›› ብሎ ተማጸናቸው፡፡ እነርሱም ‹‹ስለዚህ ሰው ነፍስ እንዳንጠፋ፣ ንጹሕም ደም በእኛ ላይ እንዳይደረግብን አይኾንም›› አሉ፡፡

ወደ ባሕሩ ለመጣል ዕጣ በተጣጣሉ ጊዜም ዕጣው በዮናስ ላይ ስለ ወጣ ነጋድያኑ ዮናስን ወደ ባሕሩ ጣሉት፡፡ ወዲያውኑ ከእግዚአብሔር ዘንድ የታዘዘ ታላቅ ዓሣ አንበሪ ዮናስን በአፉ ተቀብሎ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት አሳድሮ ወደ ነነዌ አደረሰው፡፡ እግዚአብሔር የቅል ተክልን ምሳሌ በማድረግ ቅጠሉ በመድረቁ ዮናስ ባዘነ ጊዜ ‹‹አንተ ላልደከምክበት እና በአንድ ቀን በቅሎ ላደገ ቅል ስታዝን እነሆ በታላቂቱ ነነዌ ከተማ ያሉ ከአንድ መቶ ሃያ ሺሕ በላይ ሕዝብና እንስሳቱ የእጄ ፍጥረቶች ስለ ኾኑ ያሳዝኑኛል›› በማለት ነቢዩ ዮናስም ውሸታም ላለመባል መኮብለሉ ስሕተት መኾኑን አስረድቶታል፡፡

ዮናስም ነነዌ መሬት ላይ መድረሱን ባወቀ ጊዜ ከእግዚአብሔር መሸሽ አለመቻሉን ተረዳ፤ የነነዌ ሰዎችንም ‹‹ንስሐ ግቡ›› እያለ መስበክ ጀመረ፡፡ የነነዌ ሰዎችም ንስሐ በገቡ ጊዜ እግዚአብሔር ይቅር ብሎ ከጥፋት አድኗቸዋል፡፡ ሐሰት እንዳይባልም እሳቱ እንደ ደመና ኾኖ ከላይ ታይቶአል፡፡ የታላላቁ ዛፍ ቅጠል እስኪጠወልግ ድረስ አድርቆ ለሕዝቡ አሳይቷቸዋል፡፡ ንስሐቸው በከንቱ እንዳልቀረ አስረድቷቸዋል /ትንቢተ ዮናስን በሙሉ ይመልከቱ/፡፡ ታኅሣሥ ፭ ቀን የሚነበበው የመጽሐፈ ስንክሳር ክፍል ‹‹ወበልዐ አሐደ ኀምለ›› በማለት ንስሐ ያልገቡ አንድ አገር ያህል ሰዎች በእሳቱ እንደ ጠፉ ይነግረናል፡፡

ጾመ ነነዌ የሦስት ቀን ሱባኤ ናት፤ በሦስት ቀናት ጾምና ጸሎት ንስሐ የገቡ የነነዌ ሰዎች ከጥፋት እንደ ዳኑ ዅሉ፣ በብሉይ ኪዳን አስቴር ሦስት ቀን ጾማ፣ ጸልያ በእስራኤል ላይ የመጣውን መቅሠፍት እንዲመለስ አድርጋለች /አስ.፬፥፲፭-፲፮/፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ከበዓል ስትመለስ ሕፃኑ ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስ መንገድ ላይ ጠፍቶአት ከሦስት ቀን ፍለጋ በኋላ በቤተ መቅደስ አግኝታዋለች /ሉቃ.፪፥፵፮/፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ለሄሮድስ በሰጠው ምላሽ መልስ ሦስት ቀን የሱባኤ ፍጻሜ መኾኑን ገልጿል /ሉቃ.፲፫፥፴፪/፡፡

ጾመ ነነዌ የእግዚአብሔርን ቸርነትና መሐሪነት የምናስታውስበት ጾም ነው፡፡ ይኸውም እኛ ፍጡራኑ በበደልን ጊዜ ፈጽሞ ከማጥፋት ይልቅ ምክንያት ፈልጎ እንድንድን ያደርገናል፡፡ ዮናስ ለስብከት ፈቃደኛ ባይኾን እንኳን እግዚአብሔር በተለየ ጥበቡ እንዲሔድ አድርጎታል፡፡ በእርግጥ እግዚአብሔር ሌላ የሚልከው ነቢይ አጥቶም አይደለም፤ እርሱንም ጭምር ሊያስተምረው ስለ ፈለገ እንጂ፡፡ የነነዌ ሰዎች የተነሳሕያን ምሳሌ ናቸው፡፡ ይህም ማለት ሰው ጥፋቱን አምኖ ንስሐ ከገባ እግዚአብሔር ይቅር ማለቱን አይተውም፡፡ ለዚህም ነው ዮናስን ‹‹አንተ ላልደከምክበት እና በአንድ ቀን በቅሎ ላደገ ቅል ስታዝን እነሆ በታላቂቱ ነነዌ ከተማ ያሉ ከአንድ መቶ ሃያ ሺሕ በላይ ሕዝብና እንስሳቱ የእጄ ፍጥረቶች ስለ ኾኑ ያሳዝኑኛል›› ያለው፡፡

ቀደምት የቤተ ክርስቲያን አባቶቻችን ይህን እና ሌሎች አጽዋማትን እንድንጾም የወሰኑልን ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ ሕጉ የተዘጋጀልን እንደ ነነዌ ሰዎች እኛም ጾመን፣ ጸልየን ከኀጢአታችን እንነጻ ዘንድ ነው፡፡ ዛሬ ዓለማችን በኀጢአት ማዕበል እየተናወጠች ባለችበት ወቅት እኛም እንደ ነነዌ ሰዎች ከበደላችን ብንመለስ እና ንስሐ ብንገባ ቸሩ ፈጣሪያችን እግዚአብሔር ይቅርታና ምሕረት የባሕርይ ገንዘቡ ስለ ኾነ ‹‹ወደ እኔ ተመለሱ፤ እኔም ይቅር እላችኋለሁ፤›› ይለናል፡፡

ስለኾነም በነቢዩ ዮናስ ላይ የተደረጉ ተአምራትንና ካለመታዘዝ የሚመጣ ቅጣት ቀላል አለመኾኑን በማስተዋል፣ ለነነዌ ሰዎች የወረደውን ምሕረት በመገንዘብ ለእግዚአብሔርም ኾነ ለሃይማኖት አባቶች እና ለወላጆቻችን መታዘዝ ይገባናል፡፡ ስንጾምም እግዚአብሔር አምላካችን መዓቱን በምሕረት፣ ቍጣውን በትዕግሥት መልሶ በኀጢአት ለጠፋው ዓለም ይቅርታውን ይልካል፡፡ በመጾማችን ራሳችን ከመዓትና ከመቅሠፍት ከመዳናችን ባሻገር በእኛ በደል ምክንያት አገራችን፣ ዕፀዋቱና እንስሳቱም ሳይቀር ከድርቅና ከቸነፈር ይተርፋሉና፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ኢትዮ አሜሪካውያን ሕፃናት መዓርገ ዲቁና ተቀበሉ

usa

ጥር ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን ሰሜን አሜሪካ ማእከል ዋሺንግተን ስቴት በአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል ለመዓርገ ዲቁና የሚያበቃ የአብነት ትምህርታቸውን ለሁለት ዓመታት ሲከታተሉ የቆዩ ኢትዮ አሜሪካውያን ሕፃናት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የዋሺንግተን እና ካሊፎርኒያ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከብፁዕ አቡነ ፋኑኤል መዓርገ ዲቁና ተቀበሉ፡፡

ሕፃናቱ መዓርገ ዲቁና የተቀበሉት በዓለ ጥምቀት በሲያትል ከተማ በተከበረበት ጥር ፲፬ ቀን እና የእመቤታችን በዓለ ዕረፍት በሲያትል ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን በተዘከረበት ጥር ፳፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ነው፡፡

ዲያቆናት

ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ከዲያቆናቱ ጋር

በተያያዘ ዜና ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል በማኅበረ ቅዱሳን አሜሪካ ማእከል ከሲያትል ንዑስ ማእከል በቀረበላቸው ጥሪ መሠረት የአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የትምህርትና ማሠልጠኛ ማእከል ባትል ከተማ ቅርንጫፍ ትምህርት ቤትን ጐብኝተዋል፡፡ ለተመራቂ ተማሪዎችም የአንገት መስቀል አበርክተውላቸዋል፡፡

በዕለቱ የአካባቢው ማኅበረ ካህናትና የተማሪዎቹ ወላጆች ለብፁዕነታቸው ደማቅ አቀባበል ያደረጉላቸው ሲኾን የትምህርት ቤቱ የአብነት መምህር በግእዝ እና አማርኛ ቋንቋዎች መወድስ ቅኔ፤ ተማሪዎቹም የቃል ትምህርትና ምስባክ አቅርበዋል፡፡

uu

በመርሐ ግብሩ ላይ የትምህርትና ሥልጠና ማእከሉ በሲያትል ንዑስ ማእከል ውስጥ በሲያትል፣ በቤልቪዉ እና በባትል፤ እንደዚሁም በሰሜን አሜሪካ ግዛቶች ባሉ ሦስት ከተማዎች በድምሩ በስድስት ትምህርት ቤቶች ከ፪፻ በላይ ተማሪዎችን በማስተማር ላይ እንደሚገኝ፤ በዚሁ ትልቅ ድካምና ጥረት በሚጠይቀው አገልግሎት ውስጥ ከማኅበሩ አባላት በተጨማሪ በአካባቢው የሚገኙ መምህራን፣ ካህናትና ዲያቆናት እንደዚሁም ሰባክያነ ወንጌል እና ወላጆች የሚያደርጉት አስተዋጽዖ የጎላ መኾኑ ለብፁዕነታቸው ሪፖርት ተደርጓል፡፡

በተጨማሪም በአሜሪካ ማእከል የአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል አማካይነት በውጭው ዓለም ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ተተኪ አገልጋይና ምእመናንን ለማፍራት ማኅበረ ቅዱሳን እያበረከተ ስለሚገኘው አተዋጽዖ ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡

u

ብፁዕነታቸውም ‹‹በአባቶችሽ ፈንታ ልጆች ተወለዱልሽ›› በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል ሲሰጡ ማኅበረ ቅዱሳን ከመነሻው ጀምሮ ዓላማውና ተልእኮው ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ተተኪዎችን ማፍራትና ስብከተ ወንጌልን ማስፋፋት መኾኑን እንደሚያውቁ ገልጸው አሁንም ማኅበሩ በማከናወን ላይ የሚገኘውን መንፈሳዊ አገልግሎት አድንቀዋል፡፡

በማእከሉ በተመለከቱት መልካም ተግባር በከፍተኛ ኹኔታ መደሰታቸውንና ይህ ሥራም ቤተ ክርስቲያን በዚህ ዘመን እየገጠማት ባለው ፈርጀ ብዙ ፈተና የተወሰነውን አገልግሎት ሊቀርፍ የሚችል ተግባር መኾኑን ጠቅሰው ማኅበረ ቅዱሳንን፣ የማእከሉ መምህራንን፣ ወላጆችን እና ተማሪዎችን በአጠቃላይ ዅሉንም ባለ ድርሻ አካላት ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል አመስግነዋል፡፡

በመጨረሻም በብፁዕነታቸው ቃለ ምዕዳን እና ጸሎተ ቡራኬ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ኾኗል፡፡

ምንጭ፡- በማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል