ኢትዮ አሜሪካውያን ሕፃናት መዓርገ ዲቁና ተቀበሉ

usa

ጥር ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን ሰሜን አሜሪካ ማእከል ዋሺንግተን ስቴት በአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል ለመዓርገ ዲቁና የሚያበቃ የአብነት ትምህርታቸውን ለሁለት ዓመታት ሲከታተሉ የቆዩ ኢትዮ አሜሪካውያን ሕፃናት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የዋሺንግተን እና ካሊፎርኒያ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከብፁዕ አቡነ ፋኑኤል መዓርገ ዲቁና ተቀበሉ፡፡

ሕፃናቱ መዓርገ ዲቁና የተቀበሉት በዓለ ጥምቀት በሲያትል ከተማ በተከበረበት ጥር ፲፬ ቀን እና የእመቤታችን በዓለ ዕረፍት በሲያትል ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን በተዘከረበት ጥር ፳፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ነው፡፡

ዲያቆናት

ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ከዲያቆናቱ ጋር

በተያያዘ ዜና ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል በማኅበረ ቅዱሳን አሜሪካ ማእከል ከሲያትል ንዑስ ማእከል በቀረበላቸው ጥሪ መሠረት የአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የትምህርትና ማሠልጠኛ ማእከል ባትል ከተማ ቅርንጫፍ ትምህርት ቤትን ጐብኝተዋል፡፡ ለተመራቂ ተማሪዎችም የአንገት መስቀል አበርክተውላቸዋል፡፡

በዕለቱ የአካባቢው ማኅበረ ካህናትና የተማሪዎቹ ወላጆች ለብፁዕነታቸው ደማቅ አቀባበል ያደረጉላቸው ሲኾን የትምህርት ቤቱ የአብነት መምህር በግእዝ እና አማርኛ ቋንቋዎች መወድስ ቅኔ፤ ተማሪዎቹም የቃል ትምህርትና ምስባክ አቅርበዋል፡፡

uu

በመርሐ ግብሩ ላይ የትምህርትና ሥልጠና ማእከሉ በሲያትል ንዑስ ማእከል ውስጥ በሲያትል፣ በቤልቪዉ እና በባትል፤ እንደዚሁም በሰሜን አሜሪካ ግዛቶች ባሉ ሦስት ከተማዎች በድምሩ በስድስት ትምህርት ቤቶች ከ፪፻ በላይ ተማሪዎችን በማስተማር ላይ እንደሚገኝ፤ በዚሁ ትልቅ ድካምና ጥረት በሚጠይቀው አገልግሎት ውስጥ ከማኅበሩ አባላት በተጨማሪ በአካባቢው የሚገኙ መምህራን፣ ካህናትና ዲያቆናት እንደዚሁም ሰባክያነ ወንጌል እና ወላጆች የሚያደርጉት አስተዋጽዖ የጎላ መኾኑ ለብፁዕነታቸው ሪፖርት ተደርጓል፡፡

በተጨማሪም በአሜሪካ ማእከል የአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል አማካይነት በውጭው ዓለም ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ተተኪ አገልጋይና ምእመናንን ለማፍራት ማኅበረ ቅዱሳን እያበረከተ ስለሚገኘው አተዋጽዖ ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡

u

ብፁዕነታቸውም ‹‹በአባቶችሽ ፈንታ ልጆች ተወለዱልሽ›› በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል ሲሰጡ ማኅበረ ቅዱሳን ከመነሻው ጀምሮ ዓላማውና ተልእኮው ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ተተኪዎችን ማፍራትና ስብከተ ወንጌልን ማስፋፋት መኾኑን እንደሚያውቁ ገልጸው አሁንም ማኅበሩ በማከናወን ላይ የሚገኘውን መንፈሳዊ አገልግሎት አድንቀዋል፡፡

በማእከሉ በተመለከቱት መልካም ተግባር በከፍተኛ ኹኔታ መደሰታቸውንና ይህ ሥራም ቤተ ክርስቲያን በዚህ ዘመን እየገጠማት ባለው ፈርጀ ብዙ ፈተና የተወሰነውን አገልግሎት ሊቀርፍ የሚችል ተግባር መኾኑን ጠቅሰው ማኅበረ ቅዱሳንን፣ የማእከሉ መምህራንን፣ ወላጆችን እና ተማሪዎችን በአጠቃላይ ዅሉንም ባለ ድርሻ አካላት ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል አመስግነዋል፡፡

በመጨረሻም በብፁዕነታቸው ቃለ ምዕዳን እና ጸሎተ ቡራኬ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ኾኗል፡፡

ምንጭ፡- በማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል