የስብከተ ወንጌል አገልግሎቱንና ሰባክያኑን እንደግፍ

በገጠርና ጠረፋማ አካባቢዎች የሚያገለግሉ ሰባክያነ ወንጌል

በገጠርና ጠረፋማው የአገራችን ክፍል ተበታትነው የሚኖሩ ብዙ ወገኖቻችን እውነተኛውን የወንጌል ብርሃን ሳይመለከቱ፣ ለሥላሴ ልጅነት ሳይበቁ፣ በጎውን ነገር ሳያዩ፣ ድኅነትን እንደ ናፈቁ ሞተ ሥጋ ይቀድማቸዋል፡፡

ጥቂት የእግዚአብሔርን ቃል ያወቁ ወንድሞች የምሥራቹን የእግዚአብሔርን ቃል ለማብሠር፤ ለወገኖቻቸው የወንጌል ብርሃንን ፈንጥቀው ወደ ዘላለማዊ ሕይወት ለማሸጋገር ሲሉ የበረኃው ንዳድ፣ የአራዊቱ ግርማ፣ ረኃቡና ጥሙ፣ ስቃዩና ሕመሙ ሳይበግራቸው፣ እንቅልፍ በዐይናቸው ሳይዞር የሐዋርያትን አሰር ተከትለው ከጠረፍ ጠረፍ እየተዘዋወሩ ወንጌልን ይሰብካሉ፡፡

የእናት ቤተ ክርስቲያናቸውን ርእይ በማንገብ ለወገኖቻቸው በጥምቀት የሥላሴ ልጅነትን ለማሰጠት ለቀናት በረኃውን በእግር ያቋርጣሉ፤ እነርሱ በእግር ሁለት፣ ሦስት ቀን የሚወጡ የሚወርዱበትን መንገድ ሌሎች የጥፋት መልእክተኞች (መናፍቃን) በዘመናዊ ተሽከርካሪ ገደል ኮረብታውን ጥሰው፣ በግል ሄሊኮፕተር ጭምር ያለ ችግር ቀድመው በመድረሳቸው ብቻ ወገኖቻችንን ይነጥቃሉ፤ ያልዘሩትን ያጭዳሉ፡፡ ይህም ለእኛ ሰባክያነ ወንጌል ሌላ ድካም ይኾንባቸዋል፤ ቀድመው ባለ መድረሳቸው በወገኖቻቸው ላይ የተዘራውን ክፉ አረም ለመንቀል ጊዜም ጕልበትም ይፈጃልና፡፡

እነዚያ የበረኃ ሐዋርያት ‹‹ወልድ ዋሕድ›› ብለው ሲያስተምሯቸው፣ ስለ ቅዱሳኑ ምልጃ ሲነግሯቸው፣ የእግዚአብሔርን መንግሥት መውረሻ ስለኾነችው ዳግም ልጅነትን ስለምታሰጠው አሐቲ ጥምቀት ሲያበሥሯቸው ‹‹እስከዚህ ዕድሜያችን ድረስ ስንጠብቃችሁ ነበር፤ እኛ የምናምነው አያቶቻችን የነገሩንን የቄሶች ሃይማኖት ነው፡፡ አስተምሩን፤ አጥምቁን፤›› ይሏቸዋል፡፡

ሰባክያኑ ከዚህ ያለውን አረም ነቅለው ሌሎች ወገኖቻቸው ጋር ለመድረስ ሲነሡ በክንፍ አይበሩ ነገር እንዴት ይድረሱ? ሥጋ ለባሽ ናቸውና ከመንገድ ይመለሳሉ፡፡ እነዚህ የበረኃ ሐዋርያት በአንዲት ሞተር ሳይክል እጦት ምክንያት በጊንጥና በእባብ እየተነደፉ፣ አጋዥ አጥተው ለወገኖቻቸው ቃለ ወንጌልን ሳያዳርሱ ይቀራሉ፡፡

እነዚህ ሐዋርያት ያለምንም እገዛ በረኃውን በእግር እያቋረጡ ከ፹፮ ሺሕ በላይ ወገኖችን በጥምቀት የሥላሴ ልጅነትን እንዲያገኙ ማድረግ ከተቻላቸው፣ ድካማቸውን በትንሹም ቢኾን ብንቀንስላቸው ደግሞ በመቶ ሺሕ የሚቈጠሩ ወገኖችን እንደሚያስጠምቁ የታመነ ነው፡፡

በጕዞ የደከመ የሰባክያኑን ጕልበት ለማደስ ፍቱን መድኀኒቱ ሞተር ሳይክል ነውና እኛ ከቤታችን ኾነን በጕዞ ሳንደክም አንዲት ሞተር ሳይክል በመለገስ ተራራውንና ቁልቁለቱን፣ በረኃውንና ቁሩን ከሐዋርያቱ ጋር አብረን እንውጣ፤ እንውረድ፡፡ የስብከተ ወንጌል አገልግሎቱንና ሰባክያኑን በመደገፍ የበረከቱ ተሳታፊዎች እንኹን፡፡

ሞተር

በጎ አድራጊው ምእመን የሞተር ሳይክል ስጦታ ሲያበረክቱ

ለድጋፋችሁና ሐሳቦቻችሁ በ 09 60 67 67 67 ደውሉልን

በማኅበረ ቅዱሳን የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብር