‹‹ሰው የለኝም››

በመምህር ኃይለሚካኤል ብርሃኑ

መጋቢት ፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ኃይለ ቃሉን የተናገረው በደዌ ዳኛ ተይዞ የአልጋ ቁራኛ ኾኖ ይኖር የነበረው መጻጕዕ ነው፡፡ መጻጕዕ ማለት በሽተኛ ማለት ነው፡፡ መጻጕዕ ይህንን የኀዘን ሲቃ የተሞላበት ተስፋ የመቁረጥ ምልክት የኾነውን ‹‹ሰው የለኝም›› የሚለውን አቤቱታ ያቀረበው ሳይንቅ ለጠየቀው፣ አይቶ በቸልታ ላላለፈው፣ የሰውን ድካሙን ለሚረዳ ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ እንደተረከው በኢየሩሳሌም በበጎች በር አጠገብ በዕብራይስጥ ቋንቋ ‹‹ቤተ ሳይዳ›› የምትባል አንዲት መጠመቂያ ነበረች፡፡ አምስትም መመላለሻ ነበረባት፡፡ ቤተ ሳይዳ ማለት ቤተ ሣህል (የይቅርታ ቤት) ማለት ነው፡፡ አምስት መመላለሻ የሚለውን ትርጓሜ ወንጌል እርከን ወይም መደብ ይለዋል፡፡ በእርከኑ ወይም በመደቡ ብዙ ድውያን ይተኛሉ፡፡ ከእነሱም ውስጥ የታወሩ፣ አንካሾች፣ የሰለሉ፣ ልምሹ የኾኑ፣ የተድበለበሉ በየእርከን እርከኖች ላይ ይተኛሉ፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ ውኃውን ለመቀደስ በየዓመቱ በሚወርድ ጊዜ ድምፁ እስኪያስተጋባ ድረስ ውኃው ይናወጣል፡፡ ድውያኑም በዚያ ሥፍራ ተኝተው የውኃውን መናወጥ ይጠባበቃሉ፡፡ ምክንያቱም በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ ውኃው ሲናወጥ ቀድሞ ወደ ውኃው የገባ አንድ ሰው ከደዌው ይፈወስ ነበርና፡፡

ፈውሱ በየጊዜው ከዓመት አንድ ጊዜ ይደረግ የነበረው የእግዚአብሔር ተአምራት በአባቶቻችን ጊዜ ነበር እንጂ አሁንማ የለም ብለው ድውያኑ ከማመን እንዳይዘገዩ ሲኾን፣ የድውያኑ መፈወስ አለመደጋገሙም (በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ መፈጸሙም) በኦሪት ፍጹም ድኅነት እንዳልተደረገ ለማጠየቅ ነው፡፡ በዚያም ከሠላሳ ስምንት ዓመት ጀምሮ የታመመ አንድ ሰው ነበረ፡፡ ከአልጋው ላይ ተጣብቆ ይኖር ነበር፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ወደዚያ ሰው ቀርቦ አየው፡፡ ጌታችን ክብር ይግባውና ተጨንቀን እያየ ዝም የማይለን፣ ስንቸገርም የሚረዳን ቸር አምላክ ነውና መጻጕዕ በደዌ ዳኛ በአልጋ ቁራኛ ተይዞ ለብዙ ዓመታት እንደተሰቃየ፣ ደዌው እንደጸናበት መከራውም እንደበረታበት አውቆ በርኅራኄ ቃል ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› አለው፡፡ ፈቃዱን መጠየቁ ነው፡፡

አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ፍትሐዊ ነውና ለማዳን የእያንዳንዳችን ፈቃደኝነት ይጠይቃል እንጂ ሥልጣን ስላለው፣ ክንደ ብርቱና ዅሉን ማድረግ የሚቻለው ስለኾነ ብቻ ያለ ፈቃዳችን የሚገዛን አምላክ አይደለም፡፡ በእኛ ላይ የሚያደርገውን የማዳኑን ሥራ ‹‹ልትነጻ ትወዳለህን፣ ምን እንዳደርግልህስ ትሻለህ?›› በማለት ከጠየቀ በኋላ ‹‹እንደእምነትህ ይኹንልህ፤ እንደእምነትሽ ይኹንልሽ›› እያለ በነጻነት እንድንመለላለስ ነጻነታችን ያወጀልን የፍቅር አምላክ ነው፡፡ መጻጕዕንም ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› ባለው ጊዜ እሱ ግን የሰጠው ምላሽ እጅግ የሚያሳዝን ነበር፡፡ ‹‹ጌታ ሆይ ውኃው በተናወጠ ጊዜ በመጠመቂያው ውስጥ የሚያኖረኝ ‹ሰው የለኝም› ነገር ግን እኔ ስመጣ ሳለሁ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል›› ብሎ መለሰለት፡፡ መጻጕዕ፣ ሰዎች ባጣ ጊዜ እንደሸሹት፣ በታመመ ጊዜ እንደተጸየፉት፣ ‹‹እንዴት ዋልኽ? እንዴት አደርኽ?›› የሚለው ሰው እንዳጣ፣ ወገን አልባ እንደኾነ እና ተስፋ እንደቆረጠ ለጌታችን ተናገረ፡፡

ጌታችን የልብን የሚያውቅ አምላክ ሲኾን ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› ብሎ የጠየቀበት ምክንያት አላዋቂ ሥጋን እንደተዋሐደ ለማጠየቅ ነው፡፡ አልዓዛር በሞተ ጊዜ ‹‹መቃብሩን አሳዩኝ ወዴት ነው የቀበራችሁት?›› እንዳለው ዅሉ፡፡ መጻጕዕም በምላሹ ‹‹ሰው የለኝም›› ማለቱ ኢየሱስ ክርስቶስን ሲያየው የሠላሳ ዓመት ጎልማሳ ነውና የውኃውን መናወጥ ተጠባብቆ ያወርደኛል ብሎ በማሰቡ ነው፡፡ አንድም አምስት ገበያ ሰው ይከተለው ነበርና አንዱን ሰው ያዝልኛል ብሎ ነው፡፡

ብዙዎቻችን የሕይወታችን ዋልታ በሰው እጅና በሰው ርዳታ ያለ ይመስለናል፡፡ ሰዎች ካልረዱን፣ ካልደጎሙን፣ አይዟችሁ ካላሉን፣ ከጎናችን ካልኾኑና በሰዎች ካልታጀብን ነገር ዅሉ የማይሳካልን ይመስለናል፡፡ ለዚህም ነው በሰዎች ትከሻ ላይ እንወድቅና ክንዳቸውን ተመርኩዘን እነሱ ሲወድቁ አብረን የምንወድቀው፡፡ ሲጠፉም አብረን ለመጥፋት የምንዳረገው፡፡ እስኪ ከሚደክመው ከሰው ትከሻ፣ ከሚዝለው ከሰው ክንድ እንውረድና በማይዝለውና በማይደክመው በአምላክ ክንድ ላይ እንደገፍ፡፡ እርሱ መታመኛ ነው፤ ያሳርፋል፡፡ የማይደክምም ብርቱ መደገፊያ ነው፡፡

መጻጕዕ ዅሉ ነገሩ በሰዎች እጅ ላይ ነው ብሎ ስላሰበና የሰዎች ርዳታ ስለቀረበት ተስፋ ቆርጦ ነበር፡፡ የተማመነባቸው ሰዎችም ሲርቁት ሕይወቱ ጨልሞበት ነበርና ‹‹ሰው የለኝም›› አለ (ዮሐ.፭፥፯)፡፡ የተቸገረውን ለመርዳት፣ ድሃውን ባዕለ ጸጋ ለማድረግ፣ የተጨነቀችቱን ነፍስ ለማጽናናት አማካሪ የማይሻው አምላክ ግን ወዲያውኑ ‹‹ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሒድ›› አለው፡፡ ሰውዬው (መጻጕዕ) ወዲያውኑ ዳነ፡፡ አልጋውንም ተሸክሞ ሔደ፡፡ ቀነ ቀጠሮ ሳይሰጥ፣ ይህን ያህል ክፈል ሳይል ብቻ መሻቱን ተመልክቶ በአምላካዊ ቃሉ ፈወሰው፡፡

በዮሐንስ ወንጌል ትርጓሜ እንደተገለጸው የእግዚአብሔር መልአክ የቀሳውስት፣ ውኃው የጥምቀት፣ አምስቱ እርከን የአምስቱ አዕማደ ምሥጢር፣ አምስቱ ድውያን የአምስቱ ፆታ ምእመናን ማለትም የአዕሩግ፣ ወራዙት፣ አንስት፣ ካህናት፣ መነኮሳት ምሳሌዎች ናቸው፡፡ እነዚህንም ሰይጣን የሚዋጋበት ለእያንዳንዱ እንደየድካሙ ሊያጠቃው ይሞክራልና ያንን ድል የሚነሱበትን ምሥጢር እንደሚያድላቸው ያጠይቃል፡፡ አዕሩግን በፍቅረ ንዋይ፣ ወራዙትን በዝሙት ጦር፣ አንስትን በትውዝፍት (የምንዝር ጌጥ)፣ ካህናትን በትዕቢት፣ መነኮሳትን በስስት ጦር ሰይጣን ይዋጋቸዋል፡፡ እነርሱም በጥምቀት ባገኙት ኃይል (የልጅነት ሥልጣን) ድል ያደርጉታልና የዚያ ምሳሌ ነው፡፡ ለመጻጕዕ መፈወስ የዘመድ ጋጋታ፣ የሰዎች ርዳታ አላስፈለገውም፡፡ በእግዚአብሔር ቃል ብቻ ተፈውሷል፡፡ ለዚህም ነው ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ ‹‹ችግረኛውን ከቀማኛው እጅ፤ ረዳት የሌለውንም ምስኪን ያድነዋልና፤›› (መዝ.፸፪፥፲፪) ሲል የተቀኘው፡፡ ጻድቁ ኢዮብም እንዲሁ ‹‹ረዳት (ኃይል) የሌለውን ምንኛ ረዳኸው፤›› (ኢዮ.፳፮፥፪) በማለት የእግዚአብሔርን አዳኝነት መስክሯል፡፡

የድንግል ማርያም ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ በሕይወቱ የደረሰለት ሰው እንዲህ ይባረካል፡፡ ስለዚህ ሰው የለኝም፣ ገንዘብ የለኝም፣ ሥልጣን የለኝም፣ ወገን የለኝም፣ ረዳት የለኝም በማለት ተስፋ የቆረጥን ሰዎች እግዚአብሔር ከሰውም፣ ከሥልጣንም፣ ከገንዘብም በላይ ነውና እርሱን ተስፋ አድርገን ዅል ጊዜ በስሙ መጽናናት እና የሚያስጨንቀንን ዅሉ በእርሱ ላይ መጣል እንደሚገባን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ‹‹አቤቱ የሚፈልጉህ ዅሉ በአንተ ደስ ይበላቸው፤ ሐሴትም ያድርጉ፡፡ ዅልጊዜ ማዳንህን የሚወዱ ዘወትር እግዚአብሔር ታላቅ ይኹን ይበሉ፤›› (መዝ.፵፥፲፮) እንዳለው ዅሉ ዅል ጊዜም በአምላካችን እግዚአብሔር ደስተኞች እንኹን፡፡

   ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የዐቢይ ጾም ሳምንታት (ለሕፃናት) – ክፍል ሁለት  

በልደት አስፋው

መጋቢት ፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ባለፈው ዝግጅታችን ከመጀመሪያው እሑድ እስከ ሦስተኛው እሑድ (ከዘወረደ ጀምሮ እስከ ምኵራብ) ድረስ የሚገኙትን የዐቢይ ጾም ሳምንታት የሚመለከት ትምህርት አቅርበንላችሁ ነበር፡፡ ዛሬ ደግሞ አራተኛውን የዐቢይ ጾም ሳምንት (መጻጕዕን) የሚመለከት ትምህርት ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡ መልካም ንባብ!

፬. መጻጕዕ

ልጆች! አራተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹‹መጻጕዕ›› ይባላል፡፡ መጻጕዕ ማለት በሽተኛ ማለት ነው፡፡ ይህ ዕለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት በበሽታ ተይዞ የነበረውን ሰው የፈወሰበት ዕለት ነው /ዮሐ.፭.፩-፱/፡፡

ልጆች! ቤተሳይዳ የምትባል አንዲት የጠበል መጠመቂያ ሥፍራ ነበረች፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ ወደዚያች መጠመቂያ ሥፍራ እየመጣ ውኃውን ከባረከው በኋላ ቀድሞ ገብቶ የተጠመቀ በሽተኛ ካለበት ከማንኛውም ደዌ (በሽታ) ይፈወስ ነበር፡፡ በዚያ ሥፍራ ለሠላሳ ስምንት ዓመታት ከበሽታው ለመፈወስ ብሎ ሲጠባበቅ የነበረ አንድ መጻጕዕ (በሽተኛ) ነበር፡፡ ውኃው በተናወጠ ጊዜ ሌሎች ቀድመው ገብተው እየተፈወሱ ሲሔዱ እሱ ግን ለሰላሣ ስምንት ዓመት በዚያ ቆየ፡፡

ከዚያ በኋላ ጌታችን በዚያ ሥፍራ ሲያልፍ ይህንን መጻጕዕ ተኝቶ አየው፡፡ በዚህ ጊዜ ለብዙ ዘመን እንዲሁ እንደ ነበረ አውቆ ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› ብሎ ከጠየቀው በኋላ እምነቱንና ጽናቱን አይቶ ‹‹ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሒድ›› አለው፡፡ በጌታችን ቃል ሰውዬው ወዲያውኑ ከበሽታው ዳነ፤ አልጋውንም ተሸክሞ የእግዚአብሔርን ቸርነት እየመሰከረ ሔደ፡፡ በአጠቃላይ አራተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት የመጻጕዕ ታሪክ የሚነገርበት፤ እንደዚሁም የአምላካችን ቸርነቱ፣ ይቅርታው፣ መሐሪነቱ የሚታወስበት ዕለት ነው፡፡

ልጆች! ደብረ ዘይትን የሚመለከት ትምህርት ደግሞ በሌላ ቀን እናቀርብላችኋለን፡፡ ለዛሬው ከዚህ ላይ ይቆየን፡፡ እስከዚያው ድረስ ሰላመ እግዚአብሔር ከዅላችሁ ጋር ይኹን!

በዝቋላ ገዳም አካባቢ የተነሣው የእሳት ሰደድ እየተባባሰ መኾኑ ተነገረ

001

በዝግጅት ክፍሉ

መጋቢት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት በደብረ ከዋክብት ዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም አካባቢ መጋቢት ፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ቀትር ላይ የተነሣው ከፍተኛ የእሳት ሰደድ እየተባባሰ መኾኑን የገዳሙ አባቶች ተናገሩ፡፡

እሳቱ የተነሣበት ምክንያት በግልጽ ባይታወቅም ትናንትና ረፋድ ላይ በቅርብ ርቀት ላይ ይጤስ የነበረው አነስተኛ እሳት ቀትር ላይ መባባሱንና እሳቱን ለማጥፋትም የገዳሙ መነኮሳት ከቅዳሴ በኋላ ወደሥፍራው መሔዳቸውን ከገዳሙ አባቶች መካከል አንዱ የኾኑት አባ ጥላኹን ስዩም ዛሬ ረፋድ ላይ ለዝግጅት ክፍላችን በስልክ አስታውቀዋል፡፡

‹‹ዓርብ ረቡዕ›› በሚባለው አካባቢ የነበረውን እሳት ሌሊት ላይ በቍጥጥር ሥር ለማዋል ቢቻልም ‹‹የቅዱሳን ከተማ›› በተባለው ቦታ በኩል በአዱላላ ተክለ ሃይማኖት አካባቢ ያለው ቃጠሎ እየተስፋፋ መምጣቱንና ሰደዱን ለመከላከልም አስቸጋሪ መኾኑን አባ ጥላኹን ተናግረዋል፡፡

እሳቱ ወደ ገዳሙ እንዳይጠጋ የመከላከሉ ሥራ እንደቀጠለ መኾኑን የጠቀሱት አባ ጥላኹን እሳት ለማጥፋት ከደብረ ዘይት ከተማ ወደ ገዳሙ ከሔዱ ምእመናን መካከል አንድ ወንድም ከገደል ላይ ወድቆ እንደተጎዳና በአሁኑ ሰዓትም ሕክምና እየተደረገለት እንደሚገኝ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

እንደ አባ ጥላኹን ማብራሪያ የገዳሙ መነኮሳት፤ የደብረ ዘይት እና የአካባቢው ነዋሪዎች፤ እንደዚሁም የፌደራል፣ የክልሉና የወረዳው ፖሊስ ኃይል ከትናንትና ጀምሮ እሳቱን ለማጥፋት ከፍተኛ ርብርብ በማድረግ ላይ ቢገኙም የአካባቢው መልክዐ ምድር በረኃማ፣ ቍጥቋጦ የበዛበትና ነፋስ የሚበረታበት ወጣገባ ቦታ መኾኑ ሰደድ እሳቱን በቍጥጥር ሥር ለማዋል የሚደረገውን ጥረት ከባድ አድርጎታል፡፡

በመጨረሻም ሰደዱ እየተስፋፋ ሔዶ በገዳሙ ላይ ጉዳት ከማድረሱ በፊት እሳቱን ሙሉ ለሙሉ ለማጥፋት እንዲቻል መላው ሕዝበ ክርስቲያን በሚቻላቸው ዓቅም ዅሉ ትብብር ያደርጉ ዘንድ አባ ጥላኹን ስዩም በገዳሙና በመነኮሳቱ ስም ጥሪአቸውን ያስተላልፋሉ፡፡

የዐቢይ ጾም ሳምንታት (ለሕፃናት) – ክፍል አንድ

በልደት አስፋው

የካቲት ፴ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ደኅና ናችሁ? እግዚአብሔር ይመስገን!፡፡ ልጆች! በልዩ ልዩ ምክንያት አልችል ብለን ዘግይተናል፡፡ በቅድሚያ በገባነው ቃል መሠረት ወቅቱን ጠብቀን ትምህርቱን ባለማቅረባችን እናንተን ይቅርታ እንጠይቃለን፡፡

ልጆች! የካቲት ፲፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ባቀረብንላችሁ ትምህርት ከሰባቱ አጽዋማት መካከል ዐቢይ ጾም አንዱ እንደኾነ፣ ዐቢይ ጾም ማለት ታላቅ ጾም ማለት እንደኾነ፣ ጾሙ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጾመው ጾም በመኾኑ ታላቅ እንደተባለ፣ ዕድሜአቸው ሰባት ዓመት ከኾናቸው ሕፃናት ጀምሮ ዅሉም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አማኞች ዐቢይ ጾምን እና ሌሎችንም አጽዋማት መጾም እንደሚገባቸው፣ እንደዚሁም ስምንቱ የዐቢይ ጾም ሳምንታት (እሑዶች) ስማቸው ማን ማን እንደሚባል ነግረናችሁ ነበር፡፡

ልጆች! ሰባቱ አጽዋማት ማን ማን እንደሚባሉም ጠይቀናችሁ ነበር አይደል? መልሱንስ ጠይቃችሁ ተረዳችሁ? በጣም ጥሩ ልጆች! መልሱን እናስታውሳችሁ፤ ሰባቱ አጽዋማት የሚባሉት፡-

፩. ጾመ ነቢያት

፪. ጾመ ገሃድ (ጋድ)

፫. ጾመ ነነዌ

፬. ዐቢይ ጾም

፭. ጾመ ድኅነት (ረቡዕ እና ዓርብ)

፮. ጾመ ሐዋርያት

፯. ጾመ ፍልሰታ (የእመቤታችን ጾም) ናቸው፡፡

በአሁኑ ሰዓት ዐቢይ ጾምን እየጾምን ነው፡፡ የምንገኘውም ሦስተኛው ሳምንት ላይ ሲኾን ስሙም ‹‹ምኵራብ›› ይባላል፡፡ የሚቀጥለውና አራተኛው ሳምንት ደግሞ ‹‹መጻጕዕ›› ተብሎ ይጠራል፡፡

ልጆች! በዛሬው ዝግጅታችን ከመጀመሪያው እሑድ እስከ ሦስተኛው እሑድ (ከዘወረደ ጀምሮ እስከ ምኵራብ) ድረስ የሚገኙትን የዐቢይ ጾም ሳምንታት የሚመለከት ትምህርት ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡ ትምህርቱን እንድከታተሉት በአክብሮት ጋብዘናችኋል!

፩. ዘወረደ

ልጆች! ከዐቢይ ጾም ሳምንታት መካከል የመጀመሪያው ሳምንት ‹‹ዘወረደ›› ይባላል፡፡ ዘወረደ ማለት ከላይ የመጣ፣ የወረደ ማለት ነው፡፡ ይህም አምላካችን ዓለምን ለማዳን ሲል ሥጋ መልበሱን (ሰው መኾኑን) ያመለክታል፡፡ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማይ ወርዶ፣ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ፣ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠምቆ፣ ወንጌልን ለዓለም ካስተማረ በኋላ በፈቃዱ መከራ ተቀብሎ፣ በመስቀል ተሰቅሎ፣ ሞቶ፣ ከሙታን ተነሥቶ ዓለምን አድኗል፡፡ ልጆች! የመጀመሪያው ሳምንት የአምላካችን የማዳን ሥራ በስፋት የሚነገርበት ወቅት በመኾኑ ‹‹ዘወረደ›› ተብሎ ተሰይሟል፡፡

፪. ቅድስት

ሁለተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹‹ቅድስት›› ይባላል፡፡ ቅድስት ማለት የተለየች፣ የተመረጠች፣ የከበረች ማለት ነው፡፡ ልጆች! ለምን የተለየች፣ የተመረጠች፣ የከበረች እንደተባለች ታውቃላችሁ? ቅዱስ አምላካችን እግዚአብሔር ዓለምን (ሰውን) ለመቀደስ ሲል ወደ ምድር መምጣቱንና ዐቢይ ጾምን መጾሙን ለማስረዳት ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የሰንበትን ክብር ለማስገንዘብ ነው፡፡ ሰንበት ቅድስት፣ የተለየች፣ የተመረጠች፣ የከበረች ዕለት ናት፡፡ ስለዚህም ልጆች! ሁለተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹‹ቅድስት›› ተብሎ ይጠራል፡፡

፫. ምኵራብ

ልጆች! ሦስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ደግሞ ‹‹ምኵራብ›› ይባላል፡፡ ምኵራብ ማለት አዳራሽ ማለት ነው፡፡ ምኵራብ ድሮ የነበሩ የእግዚአብሔር ሰዎች መንፈሳዊ ትምህርት ይማሩበት የነበረ  ሥፍራ ነው፡፡ በአንድ ወቅት ይህንን የጸሎት ሥፍራ ሰዎች የንግድ ቦታ አደረጉት፡፡ ይህንን ዓለማዊ ተግባር ሲፈጽሙ የነበሩትን ዅሉ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል፡፡ እናንተ ግን የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችሁት›› ብሎ ከምኵራብ አስወጣቸው፡፡ ከዚያም ቃለ እግዚአብሔር አስተማራቸው፡፡ ልጆች! የእግዚአብሔር ቤት የጸሎት ቤት እንጂ የንግድ መነገጃ ሥፍራ አለመኾኑን ከዚህ ታሪክ እንማራለን፡፡

ለዛሬው በዚህ ይቆየን፡፡ ቀጣዩን ትምህርት ደግሞ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በሚቀጥለው ዝግጅት ይዘንላችሁ እንቀርባለን፡፡ እስከዚያው ድረስ ሰላመ እግዚአብሔር ከዅላችን ጋር ይኹን!

ዐቢይ ጾም

በሊቀ ጉባኤ ቀለመወርቅ ውብነህ

የካቲት ፳፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጾም ማለት መተው መከልከል ማለት ነው፡፡ ጾም በእግዚአብሐር የተቀደሰ ተግባር ስለኾነ ወደ ቅድስና ጎዳና የሚመራ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችንም ሥርዓት ሠርታ ጾመን ከአምላካችን ጋር ኅብረት እንዲኖረን፤ መንፈሳዊ ኃይል እንድናገኝ ታደርጋለች፡፡ በጾም ወራት ከመባልዕት መከልከል ብቻ ሳይኾን ዐይን ክፉ ከማየት፣ አንደበት ክፉ ከመናገር፣ ጆሮ ክፉ ከመስማት መቆጠብ እንደሚገባው በቅዱሳት መጻሕፍት ተጽፎአል፡፡ ‹‹ይጹም ዐይን ይጹም ልሳን እዝንኒ ይጹም እምሰሚዓ ኀሡም በተፋቅሮ›› እንዲል ቅዱስ ያሬድ /ጾመ ድጓ/፡፡ በጾም ወራት ላምሮት፣ ለቅንጦት የሚበሉ ወይም ለመንፈሳዊ ኃይል ተቃራኒ የኾኑ ሥጋዊ ፍትወትን የሚያበረታቱ፣ ሥጋንና የሚያሰክሩ መጠጦችን /ዳን.፲፥፪-፫/፣ ቅቤና ወተትን ከመጠቀም መታቀብ እንደሚገባ ታዟል /መዝ.፻፰፥፳፬፣ ፩ቆሮ.፯፥፭፤ ፪ቆሮ.፮፥፮/፡፡

በብሉይ ኪዳን ጾም ከፍተኛ ቦታ ነበረው፡፡ የብሉይ ኪዳን ነቢያት ከእግዚአብሔር በሚገናኙበት ወራት እህልና ውኃ በአፋቸው አይገባም ነበር /ዘፀ.፴፬፥፳፰/፡፡ አስቴር አስቀድማ ሦስት ቀን ጾማ ጸልያ በእስራኤል ላይ የመጣውን መቅሠፍት እንዲመለስ አድርጋለች /አስቴር ፬፥፲፭-፲፮/፡፡ በዘመኑ በኃጢአት ብዛት የታዘዘው የእግዚአብሔር መዓት የሚመለሰውም ሕዝቡ በጾም ሲለምኑትና ሲማልዱት ነበር  /ዮናስ ፪፥፯-፲/፡፡ በሐዲስ ኪዳንም ጾም ሰው ሠራሽ ሕግ ሳይኾን ራሱ ክርስቶስ የሠራው ሕግ ነው /ማቴ.፬፥፪፤ ሉቃ.፬፥፪/፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም በየጊዜው ከመንፈስ ቅዱስ ትእዛዝ የሚቀበሉት በጾም በጸሎት ላይ እንዳሉ ነበር /ሐዋ.፲፫፥፪/፡፡ ለስብከተ ወንጌል የሚያገለግሉ ዲያቆናትና ቀሳውስትም የሚሾሙት በጾምና በጸሎት ነው /ሐዋ.፲፫፥፫፤ ፲፬፥፳፫/፡፡ እንደ ቆርነሌዎስ ያሉ ምእመናን ያላሰቡትን ክብር ያዩና ያገኙ የነበረውም በጾምና በጸሎት ፈጣሪያቸውን በመማጸን ነው /ሐዋ.፲፥፴/፡፡

ዐቢይ ጾም ጌታችን ከተጠመቀ በኋላ ዐርባ ቀን የጾመው፤ እኛም እንድንጾማቸው በቤተ ክርስቲያናችን ከታዘዝናቸው ሰባቱ የአዋጅ አጽዋማት አንዱ ነው፡፡ ምእመናን ጌታችን ያደረገውን ምሳሌ ተከትለን ጾሙን በየዓመቱ እንጾመዋለን፡፡ ዐቢይ ጾም ስምንት ሳምንታት (፶፭ ቀኖች) አሉት፡፡ በውስጡ ስምንት ቅዳሜዎች፣ ሰባት እሑዶች ይገኛሉ፡፡ ይኸውም ዐሥራ አምስት ቀን ማለት ነው፡፡ እነዚህ ቀናት ከጥሉላት እንጂ ከእኽል ውኃ ስለማይጦሙ የጦሙ ወራት ዐርባ ቀን ብቻ ይኾናል፡፡

ጾሙ በተለያዩ ስሞች ይጠራል፤ አንደኛ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ የጾመው በመኾኑ፣ እንደዚሁም ‹‹ዐቢይ እግዚአብሔር ወዐቢይ ኀይሉ ዐቢይ እግዚአብሔር ወብዙኅ አኰቴቱ›› /መዝ.፵፯፥፩፤ መዝ.፻፵፮፥፭/ የተባለ ጌታችን የጾመው ጾም ስለኾነ ‹‹ዐቢይ ጾም›› ይባላል፡፡ ሁለተኛ ‹‹ሁዳዴ ጾም›› ይባላል፡፡ ይህም የመንግሥት እርሻ ወይም ማንኛውም የሕዝብ ብዛት ያለበት ሥራ ሁዳድ ስለሚባል ሲኾን፣ ዐቢይ ጾምም ከአጽዋማት ዅሉ ብዙ ቀናት ስለሚጾምና ኃያሉ አምላካችን ስለጾመው ነው /አሞ.፯፥፩/፡፡ ሦስተኛ ‹‹በአተ ጾም›› ይባላል፡፡ የጾም መግቢያ፣ መባቻ ማለት ነው፡፡ አራተኛ ‹‹ጾመ ዐርባ›› ይባላል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጾመው ፵ ቀን ስለኾነ /ማቴ.፬፥፩/፡፡ አምስተኛ ‹‹ጾመ ኢየሱስ›› ይባላል፡፡ ጌታችን እርሱ ጾሞ፣ ጹሙ ብሎ ስላዘዘን፡፡ ስድስተኛ ‹‹ጾመ ሙሴ›› ይባላል፡፡ ቅዱስ ያሬድ በዘወረደ ጾመ ድጓው ‹‹ከመዝ ይቤ ሙሴ እስመ ለዓለም ሙሴኒ ይቤ በውስተ ኦሪት›› እያለ ስለዘመረ /የሰኞ ዕዝል/፡፡

ከዐቢይ ጾም ሳምንታት መካከል የመጀመሪያው ሳምንት ‹‹ዘወረደ (ዘመነ አዳም)›› ይባላል፡፡ ዘወረደ ማለት ከላይ የመጣ፣ የወረደ ማለት ነው፡፡ ይህም አምላካችን አዳምንና ልጆቹን ከሞት ለማዳን ሲል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው መኾኑንና የፈጸመውን የማዳን ሥራ ያመለክታል፡፡ ‹‹ከሰማይ ከወረደው በቀር ወደሰማይ የወጣ የለም›› ካለው ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ቃል በመነሣት ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ‹‹ዘወረደ እምላዕሉ አይሁድ ሰቀሉ ወሚመ ኢያእመሩ እግዚአ ኵሉ ዘየሐዩ በቃሉ›› በማለት በጾመ ድጓው መጀመሪያ ላይ ይህን ዕለት ገልጾታል፡፡ ትርጕሙም ‹‹አዳምን ለማዳን ከሰማይ የወረደውን አምላክ አይሁድ ሰቀሉት፤ የሰማይ ሥልጣን ያለው የዅሉ ጌታ እንደኾነም ምንም አላወቁም›› ማለት ነው፡፡ ይህም ድርሰት በቤተ ክርስቲያናችን የጾም መጀመሪያ የኾነው ዕለተ ሰንበት ዋዜማ፣ መግቢያ (መሐትው) ኾኖ ከዋዜማ በፊት ምንጊዜም በየዓመቱ ይቆማል፤ ይዘመራል፤ ይመሰገናል፡፡

በዚህ ሳምንት በተለይም እሑድና ሰኞ የሚነገሩት ውዳሴያት ከመጻሕፍተ ኦሪትና ነቢያት የተወሰዱ ናቸው፡፡ ሁለተኛም ሳምንቱ ‹‹ሙሴኒ›› በመባል ይታወቃል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ አዳምን ለማዳን ከሰማይ መውረዱንና በመስቀል መሰቀሉን ስለሚያወሳ ነው፡፡ በተጨማሪም ይህ የመጀመሪያው ሳምንት ‹‹ጾመ ሕርቃል›› ይባላል፡፡ ሕርቃል (ኤራቅሊየስ) የቤዛንታይን ንጉሥ ነበር፡፡ ይህ ሳምንት በስሙ የተጠራበት ምክንያት በዘመኑ ፋርሶች ኢየሩሳሌምን ወርረው፣ የጌታችንን መስቀል ማርከው ወስደውት ነበር፡፡ እርሱ ወደ ፋርስ ዘምቶ መስቀሉን ከእነርሱ ነጥቆ ይዞ ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሷል፡፡

ሕርቃል ከፋርሶች ጋር ከመዋጋቱ በፊት ሐዋርያት በሲኖዶሳቸው ‹‹ነፍስ የገደለ ሰው እስከ ዕድሜ ልኩ ይጹም›› ብለው ሥርዓት ሠርተዋልና ጾሙን ፈርቶ ስለነበር በኢየሩሳሌም የነበሩ ምእመናን አሳቡን ደግፈው ‹‹አንተ ጠላታችንን አጥፋልን፤ መስቀሉን አስመልስልን እንጂ የአንድ ሰው ዕድሜ ቢበዛ ሰባ፣ ሰማንያ ዓመት ነው፡፡ ጾሙን አምስት አምስት ቀን ተከፋፍለን እኛ እንጾምልሃለን›› ብለው ጾመውለታል፡፡ ይህንን መሠረት በማድረግ ያላወቁት አንድ ጊዜ ጾመው ትተውታል፡፡ ያወቁት ግን ቀድሞም ሐዋርያት ጾመውታል ብለው ሥርዓት አድርገው በዓመት በዐቢይ ጾም መጀመሪያ ላይ ጾመ ሕርቃል እያሉ የሚጾሙት ኾነዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ይህንን ሥርዓት መሠረት በማድረግ ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጾም የመጀመሪያውን ሳምንት ጾመ ሕርቃል በሚል ስም ሰይማ እንዲጾም አድርጋለች (የመጋቢት ፲ ቀን ስንክሳርን ይመልከቱ)፡፡

በቅዱስ ያሬድ ጾመ ድጓ ዘወረደ እየተባለ የሚታወቀው፣ በጾመ ዐርባው ወቅት በተለይም በመጀመሪያው ሳምንት የሚገኘው ድርሰት በነግህ በሠለስት፣ በቀትርና በሠርክ እንደዚሁም ቅዳሜና እሑድ በሌሊት የሚዘመር ነው፡፡ በውስጡም የያዘው ፍሬ ሐሳብ የጾምን፣ የጸሎትን፣ የምጽዋትንና የፍቅርን ጠቃሚነት አጕልቶ የሚያስተምር ነው፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ በዘወረደ ጾመ ድጓው ‹‹አዘዞ እግዚአብሔር ለሙሴ ወይቤሎ ሰብእከ ወላህምከ ወኵሉ ቤትከ ያዕርፉ በሰንበት፤ እግዚአብሔር ሙሴን ሕዝብህ የከብትህ መንጋህ ቤተሰብህ ዅሉ በሰንበት ቀን ከድካማቸው ይረፉ በማለት አዘዘው፤›› በማለት ሰንበት ለሰው ልጆች ብቻ ሳይኾን፣ ሕይወት ላለው ነገር ዅሉ ጸጥታና ሰላም የሰፈነባት የዕረፍት ቀን ስለመኾኗ ተናግሯል /ዘፀ.፳፥፲፤ ፳፫፥፲፪/፡፡ በዚህም ወቅቱ ‹‹ዘመነ ጾም›› ወይም ‹‹ጾመ ሙሴ›› ይባላል፡፡

በአጠቃላይ ጾምን መጾም የፈቃድ ብቻ ሳይኾን የትእዛዝም ነው፡፡ ነቢዩ ኢዩኤል ‹‹ቀድሱ ጾመ ወስብኩ ምሕላ …፤ ጾምን ያዙአጽኑ፡፡ ምሕላንም ዐውጁ፡፡ ሸማግሌዎቹን ከፈጣሪያችን ቤት ሰብስባችሁ በአንድነት ኾናችሁ ወደ እግዚአብሔር ጩኹ (ለምኑ)፤›› ብሏል /ኢዩ.፩፥፲፩፤ ፪፥፲፪፤ ፲፪፥፲፭-፲፮/፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹ወኩኑ ላእካነ ለእግዚአብሔር በጾም ወበንጽሕ፤ በጾም፣ በንጽሕና ተወስናችሁ እግዚአብሔርን አገልግሉ፤›› ብሏል /፪ቆሮ.፮፥፬-፮/፡፡ ጾም ባያስፈልግ ኖሮ ጌታችን ‹‹በምትጾሙበት ጊዜ እንደ ግብዞች አትኹኑ … ስለ ጽድቅ የሚራቡ የሚጠሙ ንዑዳን ክብራን ናቸው፤›› ባላለም ነበር /ማቴ.፭፥፮-፲፮/፡፡ ነቢዩ ዳዊትም ‹‹ጕልበቶቼ በጾም ደከሙ፤ ሥጋዬም ቅባት በማጣት ከሳ፤›› /መዝ.፻፰፥፳፬/ ማለቱ የጾምን አስፈላጊነት ያስረዳል /ዳን. ፱፥፫-፬፤ ፲፬፥፭/፡፡ በቁራኝነት አብሮ የሚኖር መንፈስ ርኩስ (ሰይጣን) እንኳን በጾም የሚወገድ መኾኑን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተናግሮአል /ማቴ.፲፯፥፳፩፤ ማር.፱፥፪/፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹ሙሽራውን ከእነሱ ለይተው የሚወስዱበት ጊዜ ይመጣል፡፡ ያን ጊዜ ይጾማሉ፤›› ያለውን የጌታን ቃል መሠረት በማድረግ ጌታችን ሞቶ ከተነሣ እና ካረገ በኋላ ጾመዋል፤ የጾምንም ሕግ ሠርተዋል /ሐዋ.፲፫፥፫/፡፡ ሠለስቱ ምዕትም ‹‹ሐዋርያት የጾሙትንና እንዲጾም የወሰኑትን መጾም ይገባል›› ብለው አጽዋማትን እንድንጾም መወሰናቸው ይህን የጌታችንን ቃል መሠረት በማድረግ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ሠራዔ ሕግ እንደመኾኑ ዐርባ ቀን ዐርባ ሌሊት ጾሞ እንጂ ዝም ብሎ ጾሙ አላለንም፡፡ ስለዚህ ጾም ትእዛዝ (ሕግ) መኾኑን ተገንዝበን ዅላችንም መጾም አለብን፡፡ ጾመን ለማበርከት ያብቃን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ይቅርታ ልትጠየቅ እንደሚገባ ተገለጸ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የካቲት ፳፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በዐድዋ ጦርነት ጊዜ በአገሩ ላይ የደረሰውን ሽንፈት ለመበቀል ሲል የኢጣልያ ፋሽስት መንግሥት ኢትዮጵያን በወረረበት ወቅት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማትና አድባራት ላይ ላደረሰው ቃጠሎ፤ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ በአባቶች ቀሳውስት፣ ዲያቆናትና መነኮሳት እንደዚሁም በምእመናን ላይ በግፍ ለፈጸመው ጭፍጨፋ የጣልያን መንግሥት እና የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን (ቫቲካን) የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን እና ኢትዮጵያን ይቅርታ መጠየቅ፤ የኢጣልያ ፋሽስት መንግሥት ከየገዳማቱና አድባራቱ የዘረፋቸውን ንዋያተ ቅድሳት፣ ጥንታውያን የብራና መጻሕፍትን እና አገራዊ ቅርሶቻችንንም መመለስ እንደሚገባቸው ተገለጸ፡፡

img_0725

በስተቀኝ እና በስተግራ አቅጣጫ፡- ጥናታዊ ጽሑፍ አቅራቢዎቹ ቀሲስ ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል እና ቀሲስ ኃይለ ኢየሱስ አለባቸው፤ ከመካከል፡- የጥናቶቹ አወያይ አቶ መስፍን መሰለ (በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ባህሎች እና ቋንቋዎች አካዳሚ ተመራማሪና የፎክሎር መምህር)

ይህ ሐሳብ የተገለጸው በማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል አዘጋጅነት የማኅበሩ አባላት፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መምህራንና ተማሪዎች፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በአጠቃላይ በርከት ያሉ ምእመናንና ምእመናት በታደሙበት በማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከል አዳራሽ የካቲት ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በተካሔደው የጥናት መርሐ ግብር ላይ ሲኾን ፣ በዕለቱ ‹‹በኢትዮጵያ ላይ የፋሽስት ኢጣልያ ወረራ እና የሮሙ ፖፕ ፒዮስ ፲፩ኛ አቋም›› እና ‹‹ቅኔ ዘዝክረ ዐድዋ›› በሚሉ አርእስት ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል፤ በጥናቶቹ ዙሪያ ከታዳሚዎች ለተነሡ ጥያቄዎችም በጥናት አቅራቢዎቹ ምላሽ ተሰጥቷል፡፡

img_0723

የመርሐ ግብሩ ተሳታፊ አባቶች እና ወንድሞች በከፊል

‹‹በኢትዮጵያ ላይ የፋሽስት ኢጣልያ ወረራ እና የሮሙ ፖፕ ፒዮስ ፲፩ኛ አቋም›› የሚለው ርእሰ ጉዳይ አቅራቢ ቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል ፋሽስት ኢጣልያ አገራችን ኢትዮጵያን በ፲፱፻፳፰ ዓ.ም በወረረበት ወቅት የጊዜው የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ፖፕ ወረራውን እና በኢትዮጵያ ላይ የተፈጸመውን ግፍ በዝምታ መመልከታቸው ተገቢ አለመኾኑን አስታውሰው ፖፑ ወረራውን ሊያወግዙ ያልቻሉበት ምክንያትም፡- በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እና በኢጣልያ መንግሥት መካከል ጥላቻ እንዳይፈጠር በመስጋታቸው፤ በዘመኑ በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን እና በካህናቱ መካከል ከባድ ተቃውሞ ስለነበር በመካከላቸው ግጭት እንዳይፈጠር በማሰባቸው እንደኾነና ዋነኛው ምክንያት ግን የኢጣልያ ኢትዮጵያን መውረር የካቶሊክ ሃይማኖትን በኢትዮጵያ ለማስፋፋት መልካም ዕድል ይፈጥራል ብለው በማመናቸው እንደኾነ በጥናታቸው አትተዋል፡፡

img_0729

ቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል (በቤተ ክርስቲያናችን በምርምር ሥራ እና በልዩ ልዩ ሓላፊነት ዘርፈ ብዙ አገልግሎት ሲሰጡ የኖሩ፣ አሁን በጡረታ ላይ የሚገኙ አባት)

ቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ አያይዘውም ፖፑ የወቅቱ የኢጣልያ ፋሽስት መንግሥት ‹‹በእግዚአብሔር ፈቃድ የተነሣ፣ በሊበራሊዝም አስተሳሰብ ያልተሞኘ መንግሥት ነው›› ብለው ያምኑ እንደነበር፤ በወቅቱ ስለወረራው ሲጠየቁ ለሚድያዎች የሰጡት ምላሽም ፖፑ ለጦርነቱ የነበራቸውን ጥሩ አቋም እንደሚያመለክት፣ ለአብነትም በአንድ ወቅት ‹‹ራስን የመከላከል ጦርነት ነው›› ሲሉ ስለ ወረራው አስፈላጊነት እንደተናገሩ፤ የአገሪቱ መንግሥት ኢትዮጵያን ሊወርር ሲዘጋጅ ሙሶሎኒ በሮም ከተማ ንግግር በሚያደርግበት ጊዜ መላው የሮም ካቶሊክ አብያተ ክርስቲያናት ደወሎች ለረጅም ሰዓት ሲደወሉ እንደነበር፤ ይህም የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ኢትዮጵያ በኢጣልያ እንድትወረር የነበራትን ፍላጎት እንደሚያመለክት ባለጥናቱ ጠቁመዋል፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም ወረራውን በገንዘብ ደግፋለች ተብላ ቤተ ክርስቲያኗ ተከሳ እንደነበር ያወሱት ቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ፣ ፋሽስት ኢጣልያ ከኢትዮጵያ ከወጣ በኋላም ‹‹እጅግ የሚያስደስት ድል›› በማለት ፖፕ ፒዮስ ፲፩ኛ ጦርነቱን ማድነቃቸው ፖፑ የፋሽስት መንግሥት እና የወረራው ደጋፊ እንደነበሩ አንዱ ማሳያ መኾኑን ልዩ ልዩ ምንጮችን ዋቢ አድርገው የፖፑን አቋም ለጉባኤው አስረድተዋል፡፡

img_0724

የመርሐ ግብሩ ተሳታፊ እናቶች እና እኅቶች በከፊል

የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ለፋሽስቱ ሠራዊት በስውር የሞራል ድጋፍ ከማድረጓ ባሻገር የኢጣልያ ፋሽስት መንግሥት በየጊዜው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አድባራትና ገዳማት ላይ ቃጠሎና የቅርስ ዘረፋ ሲያካሒድ፤ እንደዚሁም ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስን እና ብፁዕ አቡነ ሚካኤልን በግፍ ሲረሽን፤ በአባቶች ቀሳውስት፣ ዲያቆናትና ምእመናን ላይ የጅምላ ጭፍጨፋ ሲፈጽም በዝምታ መመልከቷ (ድርጊቱን አለማውገዟ) የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የወረራው ደጋፊ እንደነበረች የሚያስገነዝብ ሌላኛው ነጥብ መኾኑን በመጥቀስ ለዚህ ዅሉ በደልም የጣልያን መንግሥት እና የሮማ ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን (ቫቲካን) የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን እና የኢትዮጵያን ሕዝብ ይቅርታ መጠየቅ፤ ለጥፋታቸውም ተመጣጣኝ ካሣ መክፈል፤ ከየገዳማቱና አድባራቱ የተዘረፉ ንዋያተ ቅድሳትን፣ ጥንታውያን የብራና መጻሕፍትን እና አገራዊ ቅርሶቻችንንም ለአገራችን መመለስ እንደሚገባቸው ቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገልጸዋል፡፡ ለዚህ ሐሳብ መሳካትም የኢትዮጵያ መንግሥት፣ የቤተ ክርስቲያን አባቶች እና መላው ሕዝበ ክርስቲያን ድጋፍ እንዲያደርጉ በማሳሰብ ቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ጥናታዊ ጽሑፋቸውን አጠቃለዋል፡፡

img_0735

ቀሲስ ኃይለ ኢየሱስ አለባቸው (በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በፊሎሎጂ ትምህርት ክፍል ፫ኛ ዓመት የፒ ኤች ዲ ተማሪ)

‹‹ቅኔ ዘዝክረ ዐድዋ›› የሚለው ጥናታዊ ጽሑፍ አቅራቢ ቀሲስ ኃይለ ኢየሱስ አለባቸው ደግሞ ከአድዋ ጦርነት በፊት፣ በጦርነቱ ወቅት እና ከድሉ በኋላ የተደረጉ አንዳንድ ጥንታውያን የግእዝ ቅኔያትን ትርጕምና ምሥጢር ከታሪክ መጻሕፍት ጋር አነጻጽረው በማቅረብ በቅኔአቸው ንጉሡንና ሠራዊቱን በማበረታታት ለአገራችን ድል ማግኘት ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያበረከቱትን ከፍተኛ አስተዋጽዖ በጥናታቸው አተተዋል፡፡

አባቶቻችን በዐድዋው ጦርነት ኢጣልያን ድል ማድረግ የተቻላቸው በወታደር እና በጦር መሣሪያ ብዛት ሳይኾን በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በቅዱስ ጊዮርጊስ ተራዳዒነት መኾኑን ያስታወሱት ቀሲስ ኃይለ ኢየሱስ ‹‹አዲስ ቅኔ መቀኘት ባንችልም እንኳን አባቶቻችን የፈጸሙትን የዐርበኝነትና የድል አድራጊነት ታሪክ እያነበብን የመወያያ አጀንዳችን ልናደርገው ይገባል›› ሲሉ ትውልዱ የአባቶቹን ውለታ መርሳት እንደሌለበት አስገንዝበዋል፡፡

በመጨረሻም በጥናታዊ ጽሑፎቹ ላይ ውይይት ከተደረገ እና ከመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች ለተነሡ ጥያቄዎች በጥናት አቅራቢዎቹ ምላሽ ከተሰጠ በኋላ መርሐ ግብሩ በአባቶች ጸሎት ተፈጽሟል፡፡

የተምሮ ማስተማር ሰንበት ትምህርት ቤት ልዩ ዐውደ ጥናት አካሔደ

te

በደመላሽ ኃይለማርያም

የካቲት ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ት/ቤት የምሥረታ ታሪክ በመጀመሪያ ደረጃ ላይ የሚነሣው አንጋፋው የ‹‹ተምሮ ማስተማር›› ሰንበት ትምህርት ቤት በሚያዝያ ወር ፳፻፱ ዓ.ም የሚከበረውን ስድሳኛ ዓመት የምሥረታ በዓሉን ምክንያት በማድረግ በምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳም የሰንበት ትምህርት ቤቱ አዳራሽ የካቲት ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ልዩ ዐውደ ጥናት አካሔደ፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ዶ/ር አባ ኃይለ ማርያም መለሰ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ፤ መጋቤ ኅሩያን አባ ኤልያስ በልሁ የምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ገዳም ምክትል አስተዳዳሪ እና የሰንበት ትምህርት ቤቱ ሰብሳቢ፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ ጥሪ የተደረገላቸው ምሁራንና እንግዶች፤ የልዩ ልዩ መገናኛ ብዙኃን ጋዜጠኞች፤ የአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች ተወካዮች፤ ቀደምት የሰንበት ትምህርት ቤቱ አባላት እና በርካታ ምእመናን ታድመዋል፡፡ በዐውደ ጥናቱም ‹‹የተምሮ ማስተማር ሰንበት ትምህርት ቤት አመሠራረትና አገልግሎት›› እና ‹‹የአማርኛ መዝሙራት ታሪካዊ ዕድገትና ተግዳሮቶች›› በሚሉ አርእስት የተዘጋጁ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል፡፡ በጥናቶቹ ዙሪያ ከተሳታፊዎች ለቀረቡ ጥያቄዎችም በአቅራቢዎቹ ምላሽ ተሰጥቷል፡፡

02

የሰንበት ትምህርቱ መስማት የተሳናቸው መዘምራን በምልክት ቋንቋ መዝሙር ሲያቀርቡ

‹‹የተምሮ ማስተማር ሰንበት ትምህርት ቤት አመሠራረትና አገልግሎት›› የሚለው ጥናት አቅራቢ ኢንጂነር ከፈለኝ ኃይሉ የተምሮ ማስተማርን የአመሠራረት ታሪክ እና አገልግሎት በተለይ ከ፲፱፻፴፱ — ፲፱፻፵፱ ዓ.ም የነበረውን የሰንበት ት/ቤቱን እንቅስቃሴ በጥናታቸው ዳሰዋል፡፡ በንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት በተፈሪ መኮንን የወንዶች ትምህርት ቤት ተማሪዎች በመነጨ ‹‹ሰዎችን ለማስታረቅ›› የሚል በጎ ሐሳብ የ‹‹ተምሮ ማስተማር›› ሰንበት ት/ቤት እንደተመሠረተ ኢንጂነር ከፈለኝ ገልጸው ለምሥረታውም ዐሥራ ሁለት ወንድሞች ትልቁን ድርሻ እንደሚወስዱ ተናግረዋል፡፡ ከእነዚህ ሰዎች በተጨማሪ በቀድሞ ስማቸው አባ መዓዛ ይባሉ የነበሩት በቅርቡ ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ድርሻ የላቀ እንደነበርም ኢንጂነሩ በጥናታቸው አብራርተዋል፡፡

03

ዲ/ን ዘውዱ በላይ (አወያይ) እና ኢንጂነር ከፈለኝ ኃይሉ (ጥናት አቅራቢ)

ከዅሉም በተለየ በንጉሡ ዘመን በቤተ ክርስቲያንና በማኅበራዊ አገልግሎት ላይ ከፍተኛ ድጋፍ ሲሰጡ የነበሩትና በ፲፱፻፷፮ ዓ.ም ያለ በቂ ምክንያት በደርግ ባለሥልጣናት በግፍ የተገደሉት አቶ አበበ ከበደ ለሰንበት ት/ቤቱ መመሥረትና መጽናት ግንባር ቀደሙን ቦታ እንደሚወስዱ ጥናት አቅራቢው አስገንዝበዋል፡፡ ሰንበት ትምህርት ቤቱ በ፲፱፻፵፱ ዓ.ም ገብረ ጊዮርጊስ አጋሼ በተባሉ አባት የተሰጠው ‹‹የተምሮ ማስተማር ማኅበር›› የሚለው ስያሜ በ፲፱፻፶ ዓ.ም በንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ እንደጸደቀና ከጊዜ በኋላም ‹‹የተምሮ ማስተማር ሰንበት ት/ቤት›› የሚለው ስሙ በቅዱስ ሲኖዶስ ዕውቅና እንዳገኘ ያስታወሱት የጥናቱ አቅራቢ የሰንበት ት/ቤቱ መመሥረት ወጣቶች ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የበኩላቸውን አስተዋጽዖ እንዲያበረክቱ በር ከመክፈቱ ባሻገር ሰባክያነ ወንጌል እንዲበራከቱና ምእመናን በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ ማድረጉን ጠቁመዋል፡፡ በጥናታቸው ማጠቃለያም ሰንበት ት/ቤቱ እንዲመሠረት ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያበረከቱትን እንደ አቶ አበበ ከበደ ያሉ ባለውለታዎችን በጸሎት መዘከርና በስማቸው መታሰቢያዎችን ማዘጋጀት እንደሚገባ ኢንጂነር ከፈለኝ አሳስበዋል፡፡

01

ቀሲስ ሰሎሞን ወንድሙ

‹‹የአማርኛ መዝሙራት ታሪካዊ ዕድገትና ተግዳሮቶች›› የሚለው ጥናታዊ ጽሑፍ አቅራቢ ቀሲስ ሰሎሞን ወንድሙ በበኩላቸው የ‹‹ተምሮ ማስተማር›› ሰንበት ት/ቤት የምሥረታ እንቅስቃሴ ከተጀመረበት ፲፱፻፴፭ ዓ.ም አንሥቶ ለሰባ ዓመታት ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መስጠቱን በጥናታቸው ጠቅሰዋል፡፡ የአማርኛ መዝሙራት መዘጋጀት የጀመሩት ሰንበት ት/ቤቱ በተመሠረተበት ወቅት አካባቢ መኾኑን ያስታወሱት ጥናት አቅራቢው በወቅቱ መዝሙራቱ ከእንግሊዝኛ ወደ አማርኛ ቋንቋ በቀጥታ ተተርጕመው ዜማቸውም ሳይቀየር ይቀርቡ እንደነበር እና ይህም ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ውጪ የኾኑ መዝሙራት እንዲበራከቱ በር መክፈቱን በጥናታቸው አመላክተዋል፡፡

ያሬዳዊ ይዘታቸውን የጠበቁ የአማርኛ መዝሙራት እንደ ተምሮ ማስተማር ባሉ ሰንበት ትምህርት ቤቶች በየዘመናቱ በጥራዝ መልክ እየታተሙ ለዛሬው ትውልድ መድረሳችውንም አስገንዝበዋል፡፡ በአሁኑ ሰዓት የሚዘመሩ ጥቂት የማይባሉ መዝሙራት በሥርዓት ስለማይዘጋጁ ካሉባቸው የዘይቤ፣ የቃላት አጠቃቀም፣ የቀለም እና ሐረግ ምጣኔ ጉድለቶች ባሻገር ምሥጢርን እና ይዘትን፣ እንደዚሁም ያሬዳዊ ዜማን ከመጠበቅ አኳያም ብዙ መሥፈርቶችን እንደማያሟሉ የገለጹት ቀሲስ ሰሎሞን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም የሚቀርቡ መዝሙራት ዅሉ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ተመዝነውና ተገምግመው በተገቢው ዅኔታና በትክክለኛው መሥፈርት ሊዘጋጁ ይገባል በማለት ጥናታዊ ጽሑፋቸውን አጠቃለዋል፡፡

በዚህ ዐውደ ጥናት ሊስተናገዱ መርሐ ግብር ከተያዘላቸው ጥናታዊ ጽሑፎች መካከል በሰዓት እጥረት ምክንያት ያልቀረበው ‹‹መገናኛ ብዙኃንና የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት›› የሚለው የዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ (በአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ የጥንታውያት መዛግብት ጥናት ተባባሪ ፕሮፌሰር) ጥናት በሌላ ጊዜ በተመሳሳይ መርሐ ግብር እንደሚቀርብ የሰንበት ት/ቤቱ ምክትል ሰብሳቢ ዲ/ን ዘውዱ በላይ ለጉባኤው ተሳታፊዎች ቃል ገብተዋል፡፡

temro

ከዚህ መርሐ ግብር በተጨማሪም ከሚያዝያ ፲፭ — ፳፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በዐውደ ርዕይ እና በልዩ ልዩ መንፈሳውያን መርሐ ግብራት የሰንበት ት/ቤቱ ስድሳኛ ዓመት ምሥረታ በዓል እንደሚዘከር ከሰንበት ት/ቤቱ ጽ/ቤት ለመረዳት ተችሏል፡፡ ለብዙ ሰንበት ትምህርት ቤቶች፣ ለማኅበረ ቅዱሳንና ጽርሐ ጽዮን የአንድነት ኑሮ ማኅበር መመሥረት ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያለው ይህ አንጋፋ ሰንበት ትምህርት ቤት በስልሳ ዓመት የአገልግሎት ጉዞው ውስጥ ያበረከተውን መንፈሳዊ አገልግሎት የሚያሳዩ ተጨማሪ የዳሰሳ ጥናቶች መደረግ እንደሚገባቸው በዐውደ ጥናቱ የተገኙ አባቶችና ምሁራን ጠቁመዋል፡፡ በመጨረሻም በአባቶች ጸሎት ጠዋት የተከፈተው ይህ የዐውደ ጥናት መርሐ ግብር በአባቶች ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ አመሻሽ ላይ ተፈጽሟል፡፡

ኪዳነ ምሕረት

%e1%8a%aa%e1%8b%b3%e1%8a%95

በዲያቆን ኃይለ ኢየሱስ ቢያ

የካቲት ፲፭ ቀን ፳፻፱ .

‹‹ኪዳን›› የሚለው ቃል ‹‹ተካየደ – ተዋዋለ፤ ቃል ኪዳን ተጋባ፤ ተማማለ›› ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲኾን፣ ትርጕሙም ኪዳን፣ ውል፣ መሐላ፣ ቃል ኪዳን፣ የውል ቃል ማለት ነው /ዘዳ.፳፱፥፩፤ ኤር.፴፩፥፴፩-፴፫፤ መዝ.፹፰፥፫/፡፡ በሌላ በኩል ኪዳን የጸሎት ስም ሲኾን፣ ጌታችን ሞትን ድል አድርጎ ከተነሣ በኋላ፣ ከማረጉ በፊት ለሐዋርያት ያስተማራቸው ጸሎት ኪዳን ይባላል፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከልጇ ከወዳጇ ከጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የምሕረት ቃል ኪዳን (ውል፣ ስምምነት) የተቀበለችበት ዕለት (የክብረ በዓል ስም) ደግሞ ኪዳነ ምሕረት ይባላል፡፡

በየዓመቱ የካቲት ፲፮ ቀን የምናከብረው ይህ በዓል እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በጎልጎታ በልጇ በመቃብር ላይ ኾና ‹‹ኦ ወልድየ ወፍቁርየ እስእለከ በእንተ ዘተሰባእከ እምኔየ ወበማኅፀንየ ዘጾረተከ፤ ልጄ ወዳጃ ሆይ ከሥጋዬ ሥጋ፣ ከነፍሴ ነፍስ ነሥተህ ሰው ስለመኾንህ፤ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ስለቻለችህ ማኅፀኔ፤ ከአንተ ጋር ከአገር ወደ አገር ስለመሰደዴ መጥተህ ልመናዬን ትሰማኝ ዘንድ እለምንሃለሁ›› እያለች ስትጸልይ ጌታ እልፍ አእላፍ መላእክቱን አስከትሎ ወደእርሷ መጥቶ ‹‹ሰላም ለኪ ማርያም እምየ፤ እናቴ ማርያም ሰላም ላንቺ ይኹን! እንዳደርግልሽ የምትለምኚኝ ምንድን ነው?›› አላት፡፡ እመቤታችንም በስሟ የሚማጸኑትንና መታሰቢያዋን የሚያደርጉትን፣ ለችግረኛ የሚራሩትን፣ ቤተ ክርስቲያን የሚያንጹትን፤ ዕጣን ዘይትና መብአ ለቤተ ክርስቲያን የሚሰጡትን፤ ለእመቤታችንና ለሃይማኖታቸው ካላቸው ፍቅር የተነሣ ልጆቻቸውን በስሟ የሰየሙትን ዅሉ እንዲምርላትና ከሞተ ነፍስ እንዲያድንላት ጠየቀችው፡፡

ጌታችንም ‹‹ይህን ዅሉ እንዳደርግልሽ መሐልኩ ለኪ በርእስየ ወበአቡየ ወበመንፈስ ቅዱስ ሕያው፤ በራሴ፣ በአባቴ እና በመንፈስ ቅዱስ ማልኩልሽ›› ብሎ ቃል ኪዳን ገብቶላት ወደ ሰማይ ዐርጓል፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ በቅዳሴው ‹‹… ዳግመኛም በእናትህ በማርያም ተማፅነናል፤ ይህችውም አንተን በመውለድ እመቤታችንና የባሕርያችን መመኪያ ናት፡፡ አንተ ‹መታሰቢያሽን ያደረገ፣ ስምሽንም የጠራ፣ የዘለዓለም ድኅነትን ይድናል› ብለሃታልና …፤›› በማለት የሚማጸነው፡፡

በተአምረ ማርያም መጽሐፍ እንደተመዘገበው በዚህ ዕለት የሚታሰቡ ሁለት ተአምራት አሉ፤ ከእነዚህም አንደኛው የስምዖን ታሪክ ነው፡፡ ስምዖን የሚባል እንግዳ ተቀባይ ደግ ሰው ነበር፡፡ ሰይጣን ለምቀኝነት አያፍርምና ከዕለታት አንድ ቀን በእንግድነት ከቤቱ ገብቶ ‹‹ልጅህን አርደህ ካላበላኸኝ ሌላ ምግብ አልበላም›› አለው፡፡ በዚህ ጊዜ ስምዖን ሲያወጣና ሲያወርድ ቆየና ‹‹አብርሃም ልጁን ሰውቶ ነው የእግዚአብሔር ሰው የተባለው›› በማለት፣ ‹‹የእግዚአብሔርን እንግዳ›› ላለማሳዘን ሲል ልጁን አርዶ አቀረበለት፡፡ እንግዳ መሰሉ ሰይጣንም ሥጋውን ቅመስልኝ ብሎ ግድ አለው፡፡ ስምዖንም (በላዔ ሰብእ) አርዶ ያዘጋጀውን የልጁን ሥጋ በቀምሰ ጊዜ ሰይጣን ስላደረበት (ስለተዋሐደው) ከዚያች ሰዓት ጀምሮ ቤተሰቦቹን፣ ጎረቤቶቹንና መንገደኛውን ዅሉ ይበላ ጀመር፡፡ በአጠቃላይ ፸፰ ሰዎችን ከበላ በኋላ አንድ በቍስል የተመታ ሰው አገኘና ሊበላው ሲል ‹‹ውኃ አጠጣኝ›› ብሎ በሥላሴ፣ በቅዱስ ሚካኤል፣ በቅዱስ ገብርኤል ስም ለመነው፤ እርሱም ዝም አለው፡፡

በመጨረሻም ‹‹በድንግል ማርያም ስም›› አለው፡፡ ስምዖን የእመቤታችንን ስም በሰማ ጊዜም ወደ ልቡናው ተመልሶ ‹‹እስኪ ቃሉን ድገመው›› አለው፤ በሽተኛውም መልሶ ‹‹ስለ ድንግል ማርያም ውኃ አጠጣኝ›› ብሎ ለመነው፡፡ ያን ጊዜ ‹‹ይህችስ እንደምታስምር በልጅነቴ ሰምቻለሁ›› ብሎ ጥቂት ውኃ ሰጠው፤ ውኃው ጕሮሮውን እንኳን ሳያርስለት ‹‹ጨረስህብኝ›› ብሎ ነጥቆት ሔደ፡፡ በሌላ ቦታም አንድ ገበሬ አግኝቶ ሊበላ ሲል ገበሬው ‹‹በላዔ ሰብ የምትባል አንተ ነህ?›› ባለው ጊዜ ‹‹ለካስ አመሌን ሰው ዅሉ አውቆብኛል›› ብሎ ዋሻ ገብቶ በመጸጸት በዚያው ሞተ፡፡ ነፍሱንም መላእክተ ጽልመት መጥተው ሲወስዷት እመቤታችን ‹‹ልጄ በማይታበል ቃልህ ይህችን ነፍስ ማርልኝ?›› አለችው፡፡ ጌታችንም ‹‹ሰባ ስምንት ነፍስ ያጠፋ፣ ፈጣሪውን የካደ ሰው ይማራልን?›› አላት፡፡ እመቤታችንም ‹‹በስሜ የተጠማውን ውኃ አጥጥቶ የለምን?›› ብላ ስምዖንን (በላዔ ሰብእን) አስምራዋለች፡፡ ነፍሱንም መላእክተ ብርሃን መጥተው ወደ ገነት አስገብተዋታል፡፡

ሁለተኛው ተአምር ደግሞ ከብሮ ከኖረ በኋላ ለድህነት በተጋለጠ አንድ ምእመን ላይ የተደረገ ነው፤ ከክርስቲያን ወገን የኾነ ሀብት አግኝቶ ያጣ አንድ ሰው ነበር፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን ‹‹ከብሬ በኖርኹበት አገር ተዋርጄ አልኖርም›› ብሎ ጓዙን ጠቅልሎ ከአገሩ ወጥቶ ሲሔድ ሰይጣን ያዘነ ሰው መስሎ ደንጊያውን በምትሐት ወርቅ አስመስሎ ‹‹ሥላሴን፣ ጻድቃንን፣ ሰማዕታትንን፣ መላእክትን ካድልኝና ይህን ወርቅ እሰጥሃለሁ›› አለው፡፡ ዅሉንም ካደለትና ወርቁን ተቀብሎ ዞር ሲል ‹‹ምእመናን የሚመኩባት ድንግል ማርያምየአምላክ እናት አይደለችም› ብለህ ካድልኝ›› አለው፡፡ ሰወየውም ‹‹እርሷንስ አልክድም›› ስላው በደንጊያ ቀጥቅጦ ገደለው፡፡ መላእክተ ጽልመት የሟቹን ነፍስ ሊወስዱ ሲሉ መላእክተ ብርሃንም አብረው ቀረቡ፡፡ እመቤታችንም ጌታችንን ‹‹ልጄ ይህችን ነፍስ ማርልኝ?›› አለችው፡፡ እርሱም ‹‹ከልብኑ ይትመሐር እምየ፤ እናቴ፣ ውሻ ይማራልን?›› አላት፡፡ እመቤታችንም፡- ‹‹‹ስምሽን የጠራውን፣ መታሰቢያሽን ያደረገውን እምርልሻለሁ› ያልኸው ቃል ይታበላልን?›› አለችው፡፡ በዚህ ጊዜ ‹‹ምሬልሻለሁ›› አላት፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን ‹‹ከመረጥኳቸው ጋር ቃል ኪዳን አደረግሁ›› ባለው መሠረት ከቅዱሳን ጋር ያደረጋቸው ቃል ኪዳኖች ብዙዎች ናቸው፡፡ ከእነዚህም መካከል ከላይ በተአምራቱ እንደተመለከትነው አንዱ ለእመቤታችን የሰጠው የአማላጅነት ኪዳን ነው፡፡ ማማለድ ማለት ስለሌላው መጸለይ፣ መለመን፣ የደረሰውን ችግር እንዲወገድ ማድረግ፣ ማስማር (ይቅርታ ማሰጠት) ማለት ነው፡፡ በዚሁ መሠረት ከእግዚአብሔር በታች ከቅዱሳን ዅሉ በላይ ከፍ ከፍ ያለችና የከበረች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከእግዚአብሔር በተሰጣት የማማለድ ሥልጣን ‹‹ሰአሊ ለነ ቅድስት፤ ቅድስት ሆይ ለምኚልን›› እያሉ ለሚለምኗት ዅሉ ከእግዚአብሔር እያማለደችና እየለመነች ምሕረትን እንደምታሰጥ ቀናውንና የተመሰገነውን ሃይማኖት የምንከተል ምእመናን ዅሉ እናምናለን፡፡ ምክንያቱም ቅድስት ድንግል ማርያም የእግዚአብሔር እናትና አገልጋይ እንደመኾኗ ከዅሉም ቅዱሳን በበለጠ ለእግዚአብሔር ቅርብ ናትና፡፡ በእግዚአብሔር ዘንድም ኾነ በሰው ዘንድ ባለሟልነትን ማግኘት ወይም ቅርብ መኾን ደግሞ አንድን ጉዳይ በቀላሉ ለማስፈጸም ይጠቅማል፡፡ ለምሳሌ፡-

  • መልአኩ ቅዱስ ገብርአል በእግዚአብሔር ፊት የሚቆም ባለሟል በመኾኑ የድኅነትን ምሥጢር አብሣሪ ኾኗል /ሉቃ. ፩፥፲፱-፳፮/፡፡
  • አስቴር የንጉሡ አርጤክስስ ሚስት በመኾኗ በወገኖቿ አይሁድ የታወጀውን የሞት አዋጅ አስለውጣለች /መጽሐፈ አስቴር ፫፥፲/፡፡
  • ነቢዩ ሙሴ በእግዚአብሔር ፊት ባለሟል በመኾኑ ‹‹ይህንን ኀጢአታቸውን ይቅር በላቸው፤ ያለዚያ ግን እኔን ከጻፍከው መጽሐፍህ እባክህ ደምስሰኝ?›› በማለት ለእስራኤላውያን ምሕረትን አሰጥቷል /ዘፀ.፴፪፥፲፬/፡፡

ስለዚህ የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነትም እንደ ፀሐይ የበራ ሐቅ ነው፡፡ ይህንን እውነት ቅዱስ ያሬድ ሲመሰክር፡- ‹‹ወታስተሠርዪ ኀጢአተ ሕዝብኪ ተበውሀ ለኪ እምአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ወከመ ትኩኒ ተንከተመ ለውሉደ ሰብእ ለሕይወት ዘለዓለም፤ ለሕዝብሽ፣ ለወገኖችሽ የኃጢአት ይቅርታን ታሰጪ ዘንድ፤ ዘለዓለማዊ ሕይወትንም ለሚወርሱ ዅሉ መሸጋገሪያ ድልድይ ትኾኚ ዘንድ ከአብ ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ ዘንድ ሥልጣን አግኝተሻል›› በማለት አመስግኗታል /አንቀጸ ብርሃን/፡፡ አባ ጽጌ ድንግልም በማኅሌተ ጽጌ ድርሰታቸው፡- ‹‹ሶበሰ ኪዳንኪ ምክንያተ ድኂን ኢሀሎ ፈለገ እሳት ወደይን እም አሰጠመ ኩሎ፤ የድኅነት ምክንያት ቃል ኪዳንሽ ባይኖር ኖሮ የጥፋት እሳት፣ መርገም (ኀጢአት) ባጠፋን ነበር›› ብለዋል፡፡ አባ ሕርያቆስም በቅዳሴው፡‹‹ጥፋትን ያይደለ ይቅርታን አሳስቢ፡፡ መዓትን ያይደለ ምሕረትን አሳስቢ፡፡ ለጻድቃን ያይደለ ለኀጥአን አሳስቢ፡፡ ለንጹሐን ያይደለ ለተዳደፉት አሶስቢ፤›› ሲሉ ይማጸኗታል /ቅዳሴ ማርያም ቍ.፻፷፭-፻፸፩/፡፡

ስለዚህም ዘወትር በሥርዓተ ቅደሴአችን፡- ‹‹ድኅነትን የምንለምንሽ ክብርን የተመላሽ ቅድስት ሆይ ደስ ይበልሽ፡፡ ዅል ጊዜ ድንግል የምትኾኚ አምላክን የወለድነሽ የክርስቶስ እናት ሆይ ኀጢአታችንን ያስተሠርይልን ዘንድ ወደ ልጅሽ ወደ ወዳጅሽ ወደ ላይ ጸሎታችንን አሰርጊልን፡፡ በእውነት የጽድቅ ብርሃን የሚሆን አምላካችንን ክርስቶስን የወለድሽልን ንጽሕት ሆይ ደስ ይበልሽ፡፡ ንጽሕት ድንግል ሆይ ለነፍሳችን ይቅርታን ያደርግ ዘንድ፤ ኀጢአታችንንም ያስተሠርይልን ዘንድ ወደ ጌታችን ለምኚልን፡፡ በእውነት ለሰው ወገን አማላጅ የምትሆኝ አምላክን የወለድሽ ንጽሕት ቅድስት ድንግል ማርያም ሆይ ደስ ይበልሽ፡፡ የኀጢአታችንን ሥርየት ይሰጠን ዘንድ በልጅሽ በክርስቶስ ፊት ለምኝልን፡፡ በእውነት ንግሥት የምትኾኚ ንጽሕት ድንግል ሆይ ደስ ይበልሽ፡፡ የባሕርያችን መመኪያ ሆይ ደስ ይበልሽ፡፡ አምላካችን አማኑኤልን የወለድሽልን ሆይ ደስ ይበልሽ፡፡ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ፊት እውነተኛ አስታራቂ ሆነሽ ታስቢን ዘንድ እንለምንሻለን፡፡ ለነፍሳችን ይቅርታን ያደርግልን ዘንድ ኀጢአታችንንም ያስተሰርይልን ዘንድ፤›› በማለት እመቤታችንን እንማጸናታለን፡፡

በአጠቃላይ ‹‹ኪዳነ ተካየድኩ ምስለ ኅሩያንየ፤ ከመረጥኋቸው ጋር ቃል ኪዳን አደረግሁ፤›› በማለት በነቢዩ ቅዱስ ዳዊት አድሮ ራሱ እግዚአብሔር ከመረጣቸው አበው ነቢያት፣ ጻድቃን፣ ቅዱሳንና ሰማዕታት ጋር ቃል ኪዳን እንደ ገባ፣ እንደሚገባ ተናግሯል /መዝ.፹፰፥፫/፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹እንግዲህ እርሱ ራሱ ካጸደቀ እግዚአብሔር የመረጣቸውን ሰዎች የሚቃወማቸው ማን ነው?›› በማለት እግዚአብሔር ሰዎችን እንደሚጠራ፣ እንደሚያከብር፣ እንደሚቀድስና ቃል ኪዳን እንደሚሰጥ ነግሮናል /ሮሜ.፰፥፴፫/፡፡ ቅዱስ ዳዊት ‹‹ነኪር ነገሩ በእንቲአኪ ሀገረ እግዚአብሔር፤ የእግዚአብሔር ከተማ ሆይ ስለ አንቺ የተነገረው ነገር ድንቅ ነው፤›› /መዝ.፹፮፥፫/ በማለት እንደተናገረው እግዚአብሔር አምላካችን ለእመቤታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም የገባው ቃል ኪዳን ከቅዱሳን ቃል ኪዳን ዅሉ ልዩ ነው፡፡ ይህም እንደምን ነው ቢሉ፡-

  • ለአምላክ እናትነት የተመረጠች ልዩ እናት በመኾኗ፤
  • አምላክ ከሥጋዋ ሥጋ፣ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ ከእርሷ በመወለዱ፤
  • ከመለለዷ በፊት፣ በወለደች ጊዜ፣ ከወለደች በኋላ ምን ጊዜም ድንግል በመኾኗ፤
  • በሁለቱም ወገን (በአሳብም በገቢርም) ድንግል በመኾኗ፤
  • አማላጅነቷ የወዳጅነት ሳይኾን የእናትነት በመኾኑ፤
  • ዓለም ይድን ዘንድ የድኅነት ምክንያት አድርጎ አምላክ ስለመረጣት ነው፡፡

ስለዚህ ብዙ ከንቱ አሳቦችን ትተን፣ እንደበላዔ ሰብእ በቃል ኪዳኗ ተጠቅመን፣ ንስሐ ገብተን፣ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ተቀብለን፣ የስሙ ቀዳሽ፣ የመንግሥቱ ወራሽ ለመኾን ያብቃን፡፡ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን አማላጅነት፣ የቅዱሳን ተራዳዒነት አይለየን፡፡

ዋቢ መጻሕፍት፡-

  • መጽሐፈ ስንክሳር
  • መዝገበ ታሪክ
  • ተአምረ ማርያም
  • አማርኛ መዝገበ ቃላት
  • ክብረ ቅዱሳን

ዐቢይ ጾም

በልደት አስፋው

የካቲት ፲፩ ቀን ፳፻፱ .

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ባለፈው ሳምንት ስለ ነቢዩ ዮናስ እና ስለ ነነዌ ሰዎች የጻፍንላችሁን ታሪክ አነበባችሁት? ጎበዞች፡፡ ከታሪኩ ውስጥ ያልገባችሁ ትምህርት ካለ ከቤተ ክርስቲያን መምህራን በመጠየቅ መረዳት ትችላላችሁ፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን ደግሞ ስለ ዐቢይ ጾም አጭር ትምህርት ይዘንላችሁ ቀርበናል፤

ልጆች! ‹‹ዐቢይ ጾም›› ማለት ታላቅ ጾም ማለት ነው፡፡ ዐቢይ ጾም በቤተ ክርስቲያናችን በዐዋጅ እንዲጾሙ ከታወጁ ከሰባቱ አጽዋማት መካከል አንዱ እና ዋነኛው ነው፡፡ ጾሙ ታላቅ የተባለበት ምክንያትም ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጾመው ጾም በመኾኑ ነው፡፡

ልጆች! ይኽንን ጾም ዕድሜአቸው ሰባት ዓመት ከኾናቸው ሕፃናት ጀምሮ ዅሉም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አማኞች እንዲጾሙት የቤተ ክርስቲያናችን ሕግ ያዝዛል፡፡ እንዴት ነው ታዲያ ሰባት ዓመትና ከዚያ በላይ የኾናችሁ ሕፃናት አጽዋማትን እየጾማችሁ ነው አይደል? እየጾማችሁ ከኾነ በጣም ጎበዞች ናችሁ ማለት ነው፤ በዚሁ ቀጥሉ፡፡

ዕድሜአችሁ ለመጾም ደርሶ መጾም ያልጀመራችሁ ካላችሁ ደግሞ ከቤተሰቦቻችሁ ጋር ተመካክራችሁ እስከምትችሉበት ሰዓት ድረስ በመጾም ጾምን ከልጅነታችሁ ጀምራችሁ ተለማመዱ፤ የጾሙ ተሳታፊዎችም ኹኑ እሺ? በሕመም ምክንያት መድኀኒት የምትወስዱ ከኾነ ግን መድኀኒታችሁን ስትጨርሱ ትጾማላችሁ፡፡

ልጆች! የዘንድሮው (የ፳፻፱ ዓ.ም) ዐቢይ ጾም የሚጀመረው መቼ እንደ ኾነ ታውቃላችሁ? የካቲት ፲፫ ቀን ነው፡፡ የሚፈታው ማለትም የሚፈሰከው ደግሞ ከአምሳ አምስት ቀናት በኋላ ሚያዝያ ፰ ቀን ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ዓመት የፋሲካ በዓል ሚያዝያ ፰ ቀን ይውላል ማለት ነው፡፡

በዐቢይ ጾም ውስጥ የሚገኙት አምሳ አምስቱ ቀናት በስምንት ሳምንታት (እሑዶች) የተከፋፈሉ ናቸው፡፡ የእያንዳንዱ ሳምንት ወይም እሑድ መጠሪያ ስሞችም የሚከተሉት ናቸው፤

የመጀመሪያው ሳምንት (እሑድ) – ዘወረደ

ሁለተኛው ሳምንት (እሑድ) – ቅድስት

ሦስተኛው ሳምንት (እሑድ) – ምኵራብ

አራተኛው ሳምንት (እሑድ) – መጻጕዕ

አምስተኛው ሳምንት (እሑድ) – ደብረ ዘይት

ስድስተኛው ሳምንት (እሑድ) – ገብር ኄር

ሰባተኛው ሳምንት (እሑድ) – ኒቆዲሞስ

ስምንተኛው ሳምንት (እሑድ) – ሆሣዕና

ተብለው ይጠራሉ፡፡

የፋሲካ በዓል የሚከበርበት የመጨረሻው የዐቢይ ጾም እሑድ ደግሞ ትንሣኤ ወይም ፋሲካ ይባላል፡፡

ልጆች! እንደ እግዚአብሔር መልካም ፈቃድ እነዚህን ሳምንታት (እሑዶች) የሚመለከት ትምህርት በየሳምንቱ እናቀርብላችኋለን፡፡ እስከዚያው ድረስ ከቤተ ክርስቲያን መምህራን ወይም ደግሞ ከወላጆቻችሁ ጠይቃችሁ ሰባቱ አጽዋማት የሚባሉት ማን ማን እንደ ኾኑ አጥንታችሁ ጠብቁን እሺ?

በሉ እንግዲህ ልጆች በሌላ ዝግጅት እስከምንገናኝ ድረስ ሰላመ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይኹን፡፡

ይቆየን

የ፳፻፱ ዓ.ም ዓቢይ ጾም መግቢያን በማስመልከት ቅዱስ ፓትርያርኩ የሰጡት ቃለ ምዕዳን

የካቲት ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

%e1%8d%93%e1%89%b5%e1%88%ad%e1%8b%ab%e1%88%ad%e1%8a%ad

የተወደዳችሁ ምእመናን! የ፳፻፱ ዓ.ም ዓቢይ ጾም የካቲት ፲፫ ቀን ይገባል፡፡ የጾሙን መግባት በማስመልከትም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የካቲት ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ጠዋት የጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ የማኅበረ ቅዱሳን፣ የመንግሥት እና የግል መገናኛ ብዙኃን ጋዜጠኞች በተገኙበት በጽሕፈት ቤታቸው ቃለ ምዕዳን የሰጡ ሲኾን፣ የቅዱስነታቸውን ሙሉ ቃለ ምዕዳን እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ዘተናገረ በእንተ በአተ ጾም ዓቢይ ዘእግዚእነ ወአምላክነ ወመድኃኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘዕሥራ ምዕት ወተስዐቱ ዓመተ ምሕረት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

በአገር ውስጥና በመላው ክፍላተ ዓለም የምትገኙ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ!

ፍጥረቱን በምሕረት፣ በይቅርታና በርኅራኄ የሚጠብቅ፣ የሚመግብና የሚያስተዳድር፣ ከዅሉ በላይ የኾነ ኃያሉ አምላካችን እግዚአብሔር እንኳን ለሁለት ሺሕ ዘጠኝ ዓመተ ምሕረት መዋዕለ ጾም ዓቢይ በሰላም አደረሳችሁ!!

‹‹ቅረቡ ኀቤሁ ወያበርህ ለክሙ፣ ወኢይትኃፈር ገጽክሙ፤ ወደ እርሱ ቅረቡ ያበራላችኋልም፤ ፊታችሁም አያፍርም፤›› (መዝ.፴፬፥፭)፡፡

የሰው ልጅ ከዐራቱ ባሕርያተ ፍጥረት በተገኘ ሥጋዊ ሕይወቱ፣ የዐራቱ ባሕርያት ውጤት የኾኑትን ማለትም እኽልን ውኃን፣ ነፋስንና እሳትን የመሻት ፍላጎቱ የላቀ እንደኾነ ዅሉ፣ ከእግዚአብሔር በተገኘ መንፈሳዊ ሕይወቱም እግዚአብሔርን የመሻት ፍላጎቱ ከፍተኛ ነው፡፡

ከእግዚአብሔር የተገኘውን ይህን ሀብተ ተፈጥሮ ከሰው ባሕርይ መለየት የማይቻል በመኾኑ ሰብአዊ ፍጡር ዅሉ ከፈጣሪው ጋር ግንኙነት ለማድረግ ይጓጓል፡፡

ሰው ወደፈጣሪው ለመቅረብ ከሚፈልገው በላይ፣ ፈጣሪም ሰውን በእጅጉ ሊቀርበውና ማደርያው ሊያደርገው ይፈልጋል፤ በመኾኑም ሁለቱም ተፈላላጊ መኾናቸው በሕገ ተፈጥሮም ኾነ በቅዱስ መጽሐፍ የታወቀ ነው፡፡

ይሁን እንጂ ሁለቱም እንዳይቀራረቡ የሚያደርጉ መሠረታውያን ነገሮች እንዳሉ ዅሉ እንዲቀራረቡ የሚያደርጓቸውም አሉ፤ ሁለቱንም ሊያቀራርቡ ከሚችሉት መካከል አንዱ ጾም ነው፡፡

እግዚአብሔር በዅለመናው ንጹሕ ቅዱስ ፍጹምና ክቡር በመኾኑ ለባሕርዩ ከማይስማሙ ድርጊቶችና ከአድራጊዎቻቸው ጋር ግንኙነት ሊያደርግ አይፈቅድም፡፡

ኾኖም ንስሐ ሲገቡና ጥፋታቸውን አምነው ሲጸጸቱ በይቅርታ የሚቀበል ርኅሩኅ፣ መሐሪና ይቅር ባይ አምላክ ነው፡፡

ከዚህ አኳያ በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የሚፈጠረውን ክፍተት ለማጥበብ ብሎም ለመዝጋት ንስሐ፣ ጾምና ጸሎት ቊልፍ መሣሪያዎች ናቸው፤ እኛ ክርስቲያኖችም ጾምን የምንጾምበት ዋና ምክንያት ይኸው ነው፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት

ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ መንፈሳዊ ኃይል ያስፈልጋል፤ መንፈሳዊ ኃይል የሚገኘው ደግሞ ሥጋዊ ኃይል ሲገታ ነው፡፡ ጾም ይህን በማድረግ ከፍተኛ ሚና ይጫወታል፡፡

ጾም ኃይለ ሥጋን በመግራት ኃይለ መንፈስ እንዲበረታ ያደርጋል፤ ጾም ራሳችንን ዝቅ አድርገን ለእግዚአብሔር እንድንገዛና ለቃሉ ታዛዥ እንድንኾን ያስችለናል፤ ጾም ሰከን ብለን ስለበደላችን እንድናስብና ለንስሐ እንድንፈጥን ያደርገናል፤ ጾም የእግዚአብሔርን ቸርነት በማሰብ ፍቅሩን እንድናውቅና እንድናመልከው፣ ለሰውም ጥሩ የኾነውን ብቻ እንድናስብ ያደርገናል፡፡

እነዚህ ነገሮች በሕይወታችን ውስጥ ሥርፀት ሲያገኙ ወደ እግዚአብሐር የመቅረቡና የመገናኘቱ ዕድል ሰፊ ይኾናል፡፡ በዚህ ሕይወት ውስጥ ኾነን ስለምንሻው ነገር እግዚአብሔርን ብንጠይቅ መልሱ ፈጣን ይኾናል፡፡ ከዚህ አንጻር የነነዌ ጾም ያስገኘው ፈጣን መልስ ማስረጃችን ነው፡፡ በጾም ኃይል አማካኝነት ከፈጣሪ ጋር የተገናኙ እነሊቀ ነቢያት ሙሴ፣ ነቢዩ ዳንኤልና ዕዝራም በዚህ ተጠቃሽ መምህሮቻችን ናቸው፡፡

ርኩስ መንፈስን ድል ለማድረግ፣ ሊጀመር የታሰበውን ዓቢይ ተግባር በስኬት ለማጠናቀቅ በጾም ረድኤተ እግዚአብሔርን መጠየቅ አስፈላጊ መኾኑን ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተግባርና በትምህርት አሳይቶናል፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያትም ይህን በተግባርና በትምህርት ፈጽመውታል፤ ከዚህ አኳያ ጾምና ሃይማኖት የማይለያዩ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች መኾናቸውን መገንዘብ አያዳግትም፡፡

በመኾኑም ጾም ራሳችንን ለመቈጣጠር፤ የእግዚአብሔር ታዛዥ ለመኾን፤ ለጥያቄአችን ፈጣን መልስ ለማግኘት፤ ርኩስ መንፈስን ድል ለማድረግ፤ ከእግዚአብሔር ጋር ለመገናኘት የሚያገለግለን ሃይማኖታዊና መንፈሳዊ መሣሪያ ነው፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናን ወምእመናት

የጾም አስፈላጊነትና ውጤታማነት ከጥንት ጀምሮ በነቢያትና በሐዋርያት የታወቀ ነው፤ ከዅሉ በላይ ደግሞ እግዚአብሔር ራሱ፡- ‹‹በፍጹም ልባችሁ በጾም፣ በልቅሶና በዋይታ ወደ እኔ ተመለሱ፤ ልባችሁን እንጂ ልብሳችሁን አትቅደዱ፡፡ አምላካችሁ እግዚአብሔር ቸርና መሐሪ ነው፤ ቍጣው የዘገየ፣ ምሕረቱ የበዛ፣ ለክፋትም የተጸጸተ ነውና ወደ እርሱ ተመለሱ፡፡ በጽዮን መለከትን ንፉ፤ ጾምንም ቀድሱ (ለዩ)፤ ጉባኤውንም አውጁ፡፡ ሕዝቡንም አከማቹ፤ ማኅበሩንም ቀድሱ፤›› ብሎ ጾምን በአዋጅ እንድንጾም አዞናል፤ (ኢዩ.፪፥፲፪-፲፰)፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ርኩስ መንፈስ ሊሸነፍና ድል ሊኾን የሚችለው በጾምና በጸሎት እንደኾነ አስረግጦ አስተምሮናል፤ (ማቴ. ፲፯፥፲፬-፳፩)፡፡

ይኹንና ጾም በእግዚአብሔር ዘንድ ዋጋም፣ መልስም፣ ኃይልም ሊያሰጥ የሚችለው እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ማለትም እግዚአብሔር ባዘዘው ትእዛዝ መሠረት ሲከናወን መኾኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ እግዚአብሔር የሚፈልገው ጾም እንዴት ያለ እንደኾነ እርሱ ራሱ እንዲህ ብሎናል፤ ‹‹እኔ የመረጥሁት ጾም ይህ አይደለምን? የበደልን እሥራት ትፈቱ ዘንድ፤ የቀንበርን ጠፍር ትለቁ ዘንድ፤ የተገፉትን አርነት ትሰዱ ዘንድ፤ ቀንበሩን ዅሉ ትሰብሩ ዘንድ አይደለምን? እንጀራህን ለተራበ ትቈርስ ዘንድ፤ ስደተኞቹ ድሆችን ወደቤትህ ታገባ ዘንድ፤ የተራቆተውን ብታይ ታለብሰው ዘንድ፤ ከሥጋ ዘመድህ እንዳትሸሸግ አይደለምን? የዚያን ጊዜ ብርሃንህ እንደ ንጋት ያበራል፤ ፈውስህም ፈጥኖ ይበቅላል፤ ጽድቅህም በፊትህ ይሔዳል፡፡ የእግዚብሔርም ክብር በላይህ ኾኖ ይጠብቅሃል፤›› ብሎ ፈቃዱን ነግሮናል፤ (ኢሳ.፶፰፥፮-፰)፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት

የጾም ዓቢይ ዓላማ ለእግዚአብሔር የሚታዘዝና የተሰበረን ልብ መፍጠር፤ በጾም፣ በጸሎት፣ በንስሐ፣ በስግደት በተመስጦ፣ በአንቃዕድዎ ለእርሱ መታዘዝና መገዛት፤ እርሱንም ማምለክ ነው፡፡

ከዚህም ጋር ጥልን በይቅርታ ማስወገድ፤ ሰላምን በማረጋገጥ ፍቅረ ቢጽን ገንዘብ ማድረግ፤ ራስን መቈጣጠርና መግዛት፤ ኃይለ ሥጋን መመከት፤ ኃይለ ነፍስን ማጐልበት፤ የእግዚአብሔርን እንጂ የሰውን አለማየት፤ የርኩሳን መናፍስትን ግፊት በመቋቋም ክፉ ምኞትን ድል ማድረግ፤ ቅዱስ ቊርባንን መቀበል፤ ኅሊናን ለእግዚአብሔር መስጠት፤ ያለንን ለነዳያን ከፍለን መመጽወት የመሳሰሉትን ዅሉ ዕለታዊ ተግባራችን በማድረግ ጾሙን ልንጾም ይገባል፡፡

በመጨረሻም

የጾም ዋና ዓላማ ለእግዚአብሔር መታዘዝ እንደ መኾኑ መጠን ምድርን እንድናበጃትና እንድናለማት ያዘዘንን ትእዛዝ ተቀብለን አካባቢያችንን በማልማት አገራችንን ውብና ለኑሮ የተመቸች በማድረግ፤ እንደዚሁም ከኃጢአት መከላከያዎች መካከል ዋናውና አንዱ ያለ ዕረፍት በሥራ መጠመድ ነውና ሕዝቡ ሥራ ሳይፈታ ፈጣሪውን በጾም እያመለከ፣ የተቸገረ ወገኑን ካለው ከፍሎ እየረዳ፣ ልማትንም እያፋጠነ የአገሩንና ሰላምና ፀጥታ እየጠበቀ መዋዕለ ጾሙን እንዲያሳልፍ በእግዚአብሔር ስም መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡

ወርኀ ጾሙን አስፈጽሞ ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም ያድርሰን፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

የካቲት ፲፫ ቀን ፳፻ወ፱ ዓ.ም.

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ