ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

ሰኔ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈሰ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን::

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ስብሰባ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ ፭ ቍጥር ፻፷፬ በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው የዘንድሮዉን መደበኛ የርክበ ካህናት ስብሰባ የጉባኤው መክፈቻ ሥርዓተ ጸሎት ከተፈጸመበት ከበዓሉ ዋዜማ ከግንቦት ፲፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ጀምሮ እስከ ሰኔ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ድረ ለዐሥራ ስድስት ቀናት ያህል ባደረገው ጉባኤ ጠቀሜታ ባላቸው የአጀንዳ ነጥቦች ተወያይቶ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡

ከእነዚህ መካከል የሚከተሉት በዋናነት ይጠቀሳሉ፤

፩. የ፳፻፰ ዓ.ም የርክበ ካህናት ጉባኤን በተመለከተ ቅዱስ ፓትርያርኩ ያደረጉት የመክፈቻ ንግግር እንዳበቃ ጉባኤው ሥራውን ቀጥሏል፡፡

፪. የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ዓመታዊ ሪፖርት በጽሑፍ ቀርቦ ጉባኤው ካዳመጠ በኋላ በሪፖርቱ ላይ ውይይት በማድረግ ለወደፊቱ የሚወሰኑት ኹሉ የአፈጻጸምƒƒ‚ ችግር እንዳይደርስባቸው ክትትል ይደረግ ዘንድ ተወስኗል፡፡

፫. እስከ አሁን እየተሠራበት ያለው ቃለ ዓዋዲ የቤተ ክርስቲያናችን መተዳደሪያ ደንብ ወቅቱን ባገናዘበ መልኩ እንዲሻሻል በተሰጠው መመሪያ መሠረት የተዘጋጀው ረቂቅ ቀርቦ ምልዓተ ጉባኤው ከተነጋገረበትና ከታየ በኋላ የረቂቁ ዝግጅት በቋሚ ሲኖዶስ ታይቶ እንዲታተም ተወስኗል፡፡

፬. ስለ ቅዱስ ፓትርያርክ እንደራሴ አስፈላጊነት ጉዳይ ቅዱስ ሲኖዶስ ከተነጋገረ በኋላ የእንደራሴ አስፈላጊነት በምን ዓይነት ሕግ ላይ ተመሥርቶ መመረጥ አለበት የሚለዉን በማጥናት ለጥቅምቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የሚያቀርቡ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትን ጨምሮ ሰባት አባላት እንዲመረጡ ተደርጓል፡፡

፭. ተፈጥሮ ባስከተለው ድርቅ ምክንያት በየመጠለያው ለሚገኙ ወገኖች የዕለት ደራሽ ርዳታ፣ ለተፈናቀሉ ወገኖችም ለመልሶ ማቋቋሚያ አገልግሎት የሚውል የገንዘብና የቁሳቁስ ርዳታ ይደረግ ዘንድ ቤተ ክርስቲያን ጥሪዋን ታስተላልፋለች፤ የድርሻዋንም አስተዋፅኦ አድርጋለች፡፡

፮. በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማት የሚያገለግል ሕንፃ ƒƒመገንባት ይቻ ዘንድ ቦታ እንዲሰጥ ከገዳሙ ማኅበረ መነኰሳት የቀረበውን ጥያቄ ምልዓተ ጉባኤው የተቀበለው ስለኾነ፣ በቤተ ክርስቲኒቱ ማእከላዊ አስተዳደር በኩል ቦታ ተፈልጎ እንዲሰጥ ተዋስኗል፡፡

፯. ቅዱስ ሲኖዶስ በየአህጉረ ስብከቱ ክፍት በኾኑ መንበረ ጵጵስናዎች ብቁ የኾኑ ኤጲስ ቆጶሳትን መርጦ ለመሾም ባለው ዕቀድ መሠረት፣

ፈተናዉንና መሰናክሉን ኹሉ አልፈው ዕውቅና ያገኙትን፤

በብሔር ዓቀፍና በዓለም ዓቀፍ ትምህርት የበሰሉትን፤

የወቀውቱንም ችግር ይፈታሉ ተብለው እምነት የተጣለባቸውንና የሚጣልባቸውን፤

ለተልእኮ የሚፋጠኑትን መነኰሳት በመመርመር፣ በማጥናትና በማጣራት ውጤቱን እስከ ሰኔ ፴ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ድረስ የሚያቀርብ አስመራጭ ኰሚቴ እንዲቋቋም ተደርጓል፡፡

፰. ሀ. ብፁዕ አባ ያሬድ ሊቀ ጳጳስ የኢትዮጵያ ሱማሌ ሀገረ ስብከት ሥራን እንደያዙ በአርሲ ሀገረ ስብከት፤

ለ.ብፁዕ አባ እንጦንስ ሊቀ ጳጳስ በምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከ፤

ሐ.ብፁዕ አባ ያዕቆብ ሊቀ ጳጳስ በደቡብና ምዕራብ አፍሪካ አህጉረ ስብከት፤

መ.ብፁዕ አባ እንድርያስ ሊቀ ጳጳስ የሊቃውንት ጉባኤ የበላይ ሓላፊነቱን ሥራ እንደያዙ በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የበላይ ሓላፊ በመኾን ተመድበው እንዲሠሩ ምልዓተ ጉባኤው ተስማምቷል፡፡

፱. በውጭ ላሉት አህጉረ ስብከት ጥናት ተደርጎ በቋሚነት የሚሠሩ አባቶች እስኪመደቡ ድረስ፣

ሀ/ ሰሜን፣ ሰሜን ምሥራቅና ሰሜን ምዕራብ አውሮፓ አህጉረ ስብከት፣

ለጊዜው በብፁዕ አባ ሙሴ የደቡብ ምዕራብና የደቡብ ምሥራቅ አውሮፓ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተደርቦ እንዲሠራ፤

ለ/ አውስትራልያ ሀገረ ስብከት፣

በብፁዕ አባ ሔኖክ የምዕራብ ወለጋና የአሶሳ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተደርቦ እንዲሠራ፤

ሐ/ ምሥራቅ አፍሪካ፣ ኬንያና ጅቡቲ አህጉረ ስብከት፣

በብፁዕ አባ ዳንኤል የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተደርቦ እንዲሠራ፤

መ/ ሥራቅ አፍሪካ፣ ሰሜን ሱዳንና ግብፅ አህጉረ ስብከት፣

በብፁዕ አባ ሉቃስ በክልል ትግራይ ዞን ወልቃይት ጸገዴ ሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተደርቦ እንዲሠራ ኾኖ፣

በተጨማሪም የትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት የበላይ ሓላፊ ኾነው እንዲሠሩ፤

ሠ/ ደቡብ ሱዳን ሀገረ ስብከት፤

በብፁዕ አባ እስጢፋኖስ የጅማ፣ የኢሉባቡርና ጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተደርቦ እንዲሠራ ሲል ምልዓተ ጉባኤው በአንድ ድምፅ ተስማምቶ ወስኗል፡፡

፲. በውጭ አህጉረ ስብከት ካሉት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር ያለው የሰላሙ ንግግር ይቀጥል ዘንድ ሰላም ለማንኛውም መሠረት መኾኑ ታምኖበት ይህንኑ ሰላም ለማምጣት አስፈላጊው ጥረት ኹሉ እንዲደረግ፡፡

፲፩. ስለ አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ረዳት ሊቀ ጳጳስ ምደባ ጉዳይ ቅዱስ ሲኖዶስ ከተወያየ በኋላ በሕገ ቤተ ክርስቲያን አንቀጽ ፶ መሠረት ብፁዕ አባ ሕዝቅኤል በያዙት ሀገረ ስብከት ሥራቸው ላይ ደርበው እስከ ጥቅምት ወር ፳፻፱ ዓ.ም ድረስ የፓትርያርክ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ኾነው እንዲሠሩ ተስማምቷል፡፡

፲፪. በየሦስት ዓመቱ የሚደረገው የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ እኪኪያጅና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ምርጫ ካሉት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት መካከል በማወዳደር፡-

ሀ. ብፁዕ አባ ዲዮስቆሮስ ሊቀ ጳጳስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣

ለ. ብፁዕ አባ ሳዊሮስ ሊቀ ጳጳስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ኾነው ለሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት እንዲሠሩ በቅዱስ ሲኖዶስ ተመርጠዋል፡፡

፲፫. በሕፃናትና ቤተሰብ ጉዳይ ድርጅት ሓላፊነት በቤተ ክርስቲያናችን እየተረዱ የሚያድጉ እጓለ ማውታ ሕፃናት በየአህጉረ ስብከቱ መኖራቸው የሚታወቅ ነው፤ ይኸው የሕፃናትና የቤተሰብ ጉዳይ ድርጅት እጓለ ማውታ ሕፃናትን በማሳደግና በማስተማር ረገድ ለሀገራችንና ለቤተ ክርስቲያናችን ትልቅ አለኝታ ስለኾነ፣ አስከ አሁን ከነበረው ይዘት በበለጠ ተጠናክሮ እንዲቀጥል በቅዱስ ሲኖዶስ ተወስኗል፡፡

፲፬. የቤተ ክርስቲያናችን እምነትና ሥርዓተ አምልኮ እስከ አሁን ድረስ ተከብሮና ተጠብቆ እንደ ኖረ ኹሉ አሁንም ከመንበረ ፓትርያርክ እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ያለው የመንፈሳዊና የማኅበራዊ አገልግሎት መዋቅር በበለጠ ተጠናክሮ ይቀጥል ዘንድ መመሪያ ተሰጥቷል፡፡

፲፭. በቤተ ክርስቲያኒቱ ማእከላዊ አሰዝተዳደር ቀልጣፋና ቅንነት የሰፈነበት አሠራር እንዲኖር፣ በየደረጃው የተዘረጉትም የልማት አውታሮች የበለጠ ውጤት እንዲኖራቸው ለማስቻል፣ ከመንበረ ፓትርያርክ ሥራ አስኪያጅ ጀምሮ ኹሎችም የየአህጉረ ስብከቱ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሓላፊነት ያለባቸው ስለኾነ ተከታትለው እየሠሩ እንዲያሠሩ ተወስኗል፡፡

፲፮. በመከናወን ላይ ለሚገኘው የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ፕሮጀክት አጀማመር ኹሉም ኅብረተሰብ እጁን ሲዘረጋ እንደቆየ ኹሉ፣ አሁንም ለፕሮጀክቱ አፈጻጸም መላው ኀብረተሰብ የበኩሉን ድርሻ ይፈጽም ዘንድ ቀዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፡፡

፲፯. ከሀገራችን ኢትዮጵያ ውጭ ባሉት አንዳንድ አህጉር እየደረሰ ያለውን የተፈጥሮና ሰው ሠራሽ ችግር በጆራችን እንሰማለን፤ በዓይናችንም እናያለን፡፡ ለማስረጃም ያህል፡-

በመሬት መንቀጠቀጥ፣ በጎርፍ መጥለቅለቅና በሰደድ እሳት ዘግናኝ አደጋ የሚደርስ ኅልፈተ ሕይወት፤

በእርስበርስ የውስጥ ጦርነት የደረሰውና እየደረሰ ያለው ዕልቂት፤

የእግዚአብሔርን ህልውና በሚፈታተኑ አንዳንድ ግለሰቦች ግንዛቤ ጉድለት እየደረሰ ያለው የጦርነት አደጋ፤

በየብስ፣ በውቅያኖሶችና በሰማይ ላይ በሚበሩ አውሮፕላኖች የሚደርሰው ዘግናኝ ዕልቂትና የመሳሰሉት ከሚጠቀሱት መካከል ናቸው፡፡

ስለዚህ እግዚአብሔር አምላካችን ጉዳት ለደረሰባቸው መጽናናትን፣ መረጋጋትን እንዲሰጥልን፤ ቅን ልቡና፣ ትሑት ሰብእና ለሚጎድልባቸው የኅብረተሰብ ክፍሎችም ትዕግሥቱን፣ ርኅራኄውን እንዲያበዛልን እንጸልያለን፡፡

በመጨረሻም በሀገራችን ጎልቶ የሚታየው ድህነት እንዲወገድ፤ የተራበው፣ የተጠማው፣ የታረዘው መሠረታዊ ፍላጎቱ ተሟልቶለት እንዲኖር፤ በሀገራችን ኢተዮጵያ፣ በዓለሙም ኹሉ ሰላም እንዲሰፍን ቅዱስ ሲኖዶስ በመጸለይ ስብሰባውን በጸሎት አጠናቋል፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤

አሜን!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ

ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም

ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ሰኔ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም፡፡

፲፰ኛው የአሜሪካ ማእከል ጠቅላላ ጉባኤ ተካሔደ።

ግንቦት ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በአሜሪካ ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል ፲፰ኛ ጠቅላላ ጉባኤ በሲያትል ዋሺንግተን ቅዳሜ ግንቦት ፳ እና እሑድ ግንቦት ፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ተካሔደ።

በጉባኤው ወደ ፬፻ የሚደርሱ የማእከሉ አባላት፤ የዲሲና የአካባቢው እንዲሁም የካሊፎርንያና ምዕራብ አሜሪካ አህጉረ ስብከት ተወካዮችና የሥራ አስፈጻሚ አባላት፤ የአብያተ ክርስቲያናት አስተዳዳሪዎችና ካህናት፣ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።

ጉባኤው በጸሎተ ኪዳን በተጀመረበት ቅዳሜ ግንቦት ፳ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የማእከሉ ሰብሳቢ ዶ/ር ሕልምነህ ስንሻው የእንኳን ደኅና መጣችሁና የመክፈቻ ንግግር ካደረጉ በኋላ በማእከሉ የተተገበሩ ዋና ዋና የአገልግሎት ሥራዎችን ዘገባ አቅርበዋል። የዲሲ እና የአካባቢው ሀገረ ስብከት ዋና ጸሐፊ መልአከ ሰላም ቀሲስ ዶ/ር መሥፍን ተገኝም የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ የብፁዕ አቡነ ፋኑኤልን መልእክት ለጉባኤው ካስተላለፉ በኋላ በመልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሽፈራው “ሥራ የበዛበት ትልቅ በር” /፩ኛቆሮ. ፱፥፲፮/ በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል፡፡

በመቀጠል የማእከሉ የአገልግሎት ክፍሎች ዓመታዊ ጠቅላላ ሪፖርትና የቀጣይ ዓመት ዕድቅ ለጉባኤው ቀርቧል፡፡ በቀረበው ሪፖርትም በንዑሳን ማእከላት በርካታ ትምህርታዊ ጉባኤዎች እንደተካሔዱ፣ በልዩ ልዩ ከተሞች የማኅበረሰብ ቴሌቪዥን ፕሮግራም እንደተጀመረ፣ ለገዳማት እና አብነት ትምህርት ቤቶች፣ እንዲሁም ኢአማንያንን ለማስተማርና ለማስጠመቅ ለተዘረጋው የስብከተ ወንጌል ፕሮጀክት ከአባላት እና ከምእመናን የተሰበሰበ የእርዳታ ገንዘብ ወደ ዋናው ማእከል እንደተላከ ተገልጿል።

የማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከል ተወካይ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩም የዋናውን ማእከል መልእክት እና ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት ከጉባኤው ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ከመስጠታቸው በተጨማሪ የተሐድሶ መናፍቃንን እንቅስቃሴና ወቅታዊ ጉዳዮችን በማስመልከት ሰፊ ማብራሪያ አቅርበዋል።

በሁለቱ ቀናት ጉባኤ ላይ በሲያትል ንዑስ ማእከል የአቡነ ጎርጎርዮስ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች ውዳሴ ማርያምና ሰዓታት በንባብና በዜማ፤ የጸሎተ ቅዳሴ ተሰጥኦና ምስባክ፤ እንደዚሁም የአብነት ትምህርትን አሰጣጥና ሒደት የሚያሳይ ሥርዓተ ማኅሌት፣ ቅኔ፣ የመጻሕፍት ትርጓሜ እና የተለያዩ መንፈሳዊ ዝግጅቶችን አቅርበዋል።

በተጨማሪም የሲያትል ንዑስ ማእከል የአገልግሎት ተሞክሮዉን ለጉባኤው ያካፈለ ሲኾን፣ የማእከሉ የአገልግሎት ክፍሎች የበጀት ሪፖርትም ለጉባኤው ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል። ከስድስት ወር በኋላ የማእከሉ የዕቅድ ክለሳ እንደሚደረግም በጉባኤው ተገልጿል።

እንዲሁም ዝክረ አበው በሚል መርሐ ግብር የሊቀ ጉባኤ አባ አበራ ሰባተኛ ዓመት የዕረፍት መታሰቢያ በማስመልከት የተዘጋጀ ፊልም ለእይታ በቅቷል።

በዕለቱ ላለፉት ሁለት ዓመታት ማዕከሉን ይመራ የነበረው የሥራ አስፈጻሚ የሥራ ዘመን በመፈጸሙ፣ ለሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት ማእከሉን በሥራ አስፈጻሚነት የሚመሩ ፲፫ አባላት በጸሎትና በዕጣ ተመርጠዋል።

በጉባኤው ማጠቃለያ በማእከሉ ፲፰ኛ ጠቅላላ ጉባኤ አዘጋጅ ኮሚቴ የዝግጅቱ ሒደትና በሲያትል ከተማ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት የሰበካ ጉባኤ አባላት፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶችና ምእመናን በልዩ ልዩ መንገድ ያበረከቱት ከፍተኛ አገልግሎት በዝርዝር የቀረበ ሲኾን ይህ አሳታፊነትና ከአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ጋር በቅንጅት የመሥራት ልምድ ለሌሎች ንዑሳን ማእከላትና ግንኙነት ጣቢያዎች ያለው አርአያነት የጎላ መኾኑ ተገልጿል።

በመጨረሻም ፲፱ኛው የማእከሉ ጠቅላላ ጉባኤ በቦስተን፣ ፳ኛው ጠቅላላ ጉባኤ ደግሞ በቨርጂንያ እንዲካሔድ ተወስኖ ጠቅላላ ጉባኤው በዝማሬ እና በጸሎት ተጠናቋል።

የቅዱስ ያሬድን ፲፭፻፫ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ የቅኔ ውድድር ተካሔደ፡፡

ግንቦት ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በጎንደር ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ት/ቤተፐች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በጎንደር ማእከል አዘጋጅነት ግንቦት ፲፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የቅዱስ ያሬድን ፲፭፻፫ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ በጎንደር ከተማ በርእሰ አድባራት ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን የቅኔ ውድድር ተካሔደ፡፡

የውድድሩ ተሳታፊ ጉባኤ ቤቶች፡- የደብረ ፀሐይ ቍስቋም ማርያም፣ የደብረ ምሕረት አቡን ቤት ቅዱስ ገብርኤል፣ የቀዳሜ አድባራት አበራ ጊዮርጊስ፣ የመካነ ሕይወት ፊት አቦ እና የደብረ ገነት አዘዞ ቅዱስ ሚካኤል ቅኔ ጉባኤ ቤቶች ሲኾኑ፣ መምህራኑ የመረጧቸው ደቀ መዛሙርትም ጉባኤ ቤቶቹን ወክለው ለውድድር ቀርበዋል፡፡

ውድድሩን በዳኝነት የመሩትም መምህር ፍቅረ ማርያም የመንበረ መንግሥት መድኃኔ ዓለም የ፬ቱ ጉባኤያት ምክትል መምህር፣ ሊቀ ብርሃናት ኤልያስ አድማሴ በዐቢየ እግዚእ ኪዳነ ምሕረት የብሉይ ኪዳን መምህር እና መምህር ቃለ ሕይወት በመካነ ነገሥት ግምጃ ቤት የሐዲስ ኪዳን መምህር ሲኾኑ የውድድሩ መሥፈርቶችም አንደኛ የቅኔው ምሥጢር፣ ሁለተኛ የዜማው ልክ፣ ሦስተኛ ገቢር ተገብሮ አገባብ፣ አራተኛ የቃላት አመራረጥ እና አምስተኛ የጊዜ አጠቃቀም ናቸው፡፡ እያንዳንዱ መሥፈርት ፳፣ ባጠቃላይም ፻ ነጥቦችን የያዘ ሲኾን ለእያንዳንዱ ተወዳዳሪም የ፲፭ ደቂቃ የማቅረቢያ ጊዜ ተሰጥቶታል፡፡

በውድድሩ ከአንደኛ አስከ ሦስተኛ ደረጃ የያዙት የወንጌል አንድምታ ትርጓሜ መጻሕፍትን፤ አራተኛና አምስተኛ የወጡት ደግሞ የትንቢተ ኢሳይያስን አንድምታ ትርጓሜ መጽሐፍ ተሸልመዋል፡፡ ይኸውም ቅኔ ተምረናል በቃን ብለው እንዳያቆሙ እና ቀጣይ መጻሕፍትን እንዲማሩ ለማሳሰብ ነው፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የማእከሉ ሰብሳቢ መምህር ዓለማየሁ ይደግ እንደተናገሩት የውድድር መርሐ ግብሩ የተዘጋጀበት ዓላማ በጉባኤ ቤቶች መካከል መልካም የሆነ የውድድር መንፈስ እንዲኖር፣ ተማሪዎቹ ራሳቸውን እንዲፈትሹ ለማድረግ፣ የቅኔ ትምህርት በማኅበረሰቡ ዘንድ እንዲታወቅ፣ የበታቾቻቸውን ለማነሣሣት እና በዋናነት ቅዱስ ያሬድን ለመዘከር ነው፡፡

የጎንደር ከተማ ወረዳ ቤተ ክህነት ሊቀ ካህናት ሊቀ አእላፍ ጥበበ አወቀ በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው እንደዚህ ዓይነቱ መርሐ ግብር እየቀዘቀዘ የመጣውን የአብነት ትምህርት በተለይ የቅኔ ትምህርት እንደሚያጠናክር ጠቅሰው ይህም ማኅበረ ቅዱሳንን እንደሚያስመሰግነው ገልጸዋል፡፡ አያይዘውም ለደቀ መዛሙርቱ አባቶቻችን ይህን ትምህርት በእግዚአብሔር ኃይል ጸንተው፣ ኮቸሮ በልተው፣ በውሻ ተበልተው አቆይተውናል፤ እኛም ጠብቀን ለትውልድ ማቆየት ይኖርብናል ሲሉ ተናግረዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ በስድስቱም ጉባኤ ቤቶች የሚገኙ በርካታ የአብነት ተማሪዎች እና በርካታ ምእመናን የተገኙ ሲኾን፣ ከምእመናኑም ይህ የቅኔ ትምህርት እንዲስፋፋ ሰፊ ትኩረት ተሰጥቶት ሊሠራ እንደሚገባው አስተያየት ተሰጥቷል፡፡

የጎንደር ማእከል መዘምራንም ቅዱስ ያሬድን የሚዘክሩ የሰማይ ምስጋና የሚል የንስሐ መዝሙር እና ያሬድ ማኅሌታይ ለእግዚአብሔር ካህኑ የሚል ወረብ አቅርበዋል፡፡

የመርሐ ግብሩ መምህር በጽሐ ዓለሙ በመንበረ መንግሥት መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን የ፬ቱ ጉባኤያት ምክትል መምህር በአብነት ትምህርት ቤት ሦስት ዓይነት ተማሪ አለ፤ እነሱም፡- እግረ ተማሪ፣ ልብሰ ተማሪ እና ልበ ተማሪ ናቸው ካሉ በኋላ ኹላችንም ልበ ተማሪን ኾነን ትምህርታችንን በሚገባ መማር አለብን ብለዋል፡፡

በመጨረሻም በአባቶች ጸሎት መርሐ ግብሩ ተጠናቋል፡፡ ይህ መርሐ ግብር በፋና ኤፍ ኤም 98.1 የሬድዮ ጣቢያም የሚዲያ ሽፋን ማግኘቱ የሚታወስ ነው፡፡

የአዳማ ማእከል የሕክምና አገልግሎት ሰጠ፡፡

ግንቦት ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በአዳማ ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአዳማ ማእከል የቅዱሳት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል በዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ለሚገኙ አባቶችና እናቶች መነኮሳት እንዲሁም ለአብነት ተማሪዎች ግንቦት ፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የሕክምና አገልግሎት ሰጠ፡፡

በሕክምና አገልግሎቱም በአዳማ ማእከል፣ በደብረ ዘይት ወረዳ ማእከልና በአዱላላ ግንኙነት ጣቢያ የሚገኙ ስፔሻሊስት ሐኪሞች፣ ሜዲካል ዶክተሮች፣ የጤና መኮንኖች፣ የላቦራቶሪ ቴክኒሻኖች እና የአዳማ ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ ግቢ ጉባኤ የሕክምና ተማሪዎች በአጠቃላይ ፴፰ የሕክምና ባለሞያዎች ተሳትፈዋል፡፡

በሕክምና አገልግሎቱም ለገዳሙ መነኮሳት እና አብነት ተማሪዎች ሙሉ የጤና ምርመራና የመድኃኒት ድጋፍም ተደርጓል፡፡ ለአባቶች መነኮሳትና ለእናቶች መነኮሳይያት የስኳር፣ የደም ግፊት እና የዓይን ምርመራ ተደርጎላቸዋል፡፡ የመድኃኒት አቅርቦቱም ከዋናው ማእከል ቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል እና ከአንድ በጎ አድራጊ ወንድም የተገኘ ነው፡፡ የአዳማ ኢዮር ክሊኒክ የመድኃኒትና የሕክምና መመርመሪያ መሣሪያ ከማቅረቡ ባሻገር የክሊኒኩ ስፔሻሊስት ሐኪሞችም ከፍተኛ አገልግሎት ፈጽመዋል፡፡

በዕለቱ ሕክምና የተደረገላቸው አባቶች መነኮሳት፣ እናቶች መነኮሳይያትና የአብነት ተማሪዎች ከ፪፻፶ የሚበልጡ ሲኾን፣ ከሕክምናው በተጨማሪ ለአብነት ተማሪዎች የግልና የአካባቢን ጤና አጠባበቅ የተመለከተ ሥልጠና በጤና ባለሞያዎች ተሰጥቷቸዋል፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ በአዳማ ማእከል የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል ለአብነት ተማሪዎች የተዘጋጀው አልባሳት፣ የገላና የልብስ ሳሙና በገዳሙ በኩል ለአብነት ተማሪዎቹ እንዲከፋፈል ተደርጓል፡፡

የገዳሙ አባቶች፣ እናቶች መነኮሳትና እና የአብነት ተማሪዎቹ በተደረገላቸው የሕክምና፣ የአልባሳት እና የጤና መጠበቂያ ድጋፍ እጅግ መደሰታቸውን ገልጸው ማኅበረ ቅዱሳን በገዳማት ላይ እየሠራ ያለው አገልግሎት የሚያስመሰግነው መኾኑንና ይህንንም ሁልጊዜ ሲያስታውሱት እንደሚኖሩ በመጥቀስ ማኅበሩ በገዳማት ላይ የሚያደርገውን አገልግሎት አጠናክሮ እንዲቀጥል በማሳሰብ ማኅበሩን ያስፋልን ይጠብቅልን በማለት መርቀው የሕክምና ቡድኑን በቡራኬና በጸሎት አሰናብተዋል፡፡