limena

የጎዳና ላይ ልመና የቤተ ክርስቲያን ገጽታ የጠቆረበት ሕገ ወጥ ተግባር

 

ዲ/ን ማለደ ዋስይሁን

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የነበራትን መተዳደሪያ በደርግ ዘመን ሙሉ ለሙሉ ማለት በሚያስችል ደረጃ ማጣቷ ይታወቃል፡፡ ይህ በመሆኑ ለብዙ ደካማ ገጽታዎች መፈጠር ምክንያት ሆኗል፡፡ አጥቢያዎች ለካህናት ደሞዝ፣ ለንዋየ limenaቅድሳት መግዣ፣ በአጠቃላይ ለአገልግሎቱ መስፋትና ማደግ የሚያስፈልገውን መተዳደሪያ ገንዘብ፣ ቁስ፣ ጉልበት ለማግኘት ከምእመናን ገንዘብ መለመን ግድ ሆኖባቸው ቆይቷል፡፡

 

ቤተክርስቲያን አስቀድሞም መተዳደሪያዋን የምታገኘው ቤታቸው ከሆነችላቸው ከተገልጋዮቹ ካህናትና ምእመናን ነው፡፡ አማኞች ዐሥራት በኩራት ማውጣት ሃይማኖታዊ ግዴታቸው ነው፡፡ ይሁን እንጂ በዚያ ደረጃ የምእመናን ተሳትፎ ባልተሟላበት ሁኔታ አገልግሎቱ እንዲቀጥል የሚፈልጉ የቤተክርስቲያን ቤተሰቦች ገንዘብ በመስጠት በመሰብሰብ የአጥቢያቸውን አገልግሎት የሰመረ ያደርጋሉ፡፡

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎቷን በማስፋት፣ በማሳደግ ረገድ ነገሥታቱን ጨምሮ በሀገሪቱ ትልቅ ክብርና ስም ከነበራቸው ልጆቿ ጀምሮ የሚበረከትላትን መባዕ ማለትም ገንዘብ፣ መሬት፣ ወርቅ፣ ብር ወዘተ ስትጠቀም ኖራለች፡፡ በኋላ ዘውዳዊ ሥርዓቱ እንዲጠፋ ሲደረግ ቤተክርስቲያን መተዳደሪያዋ ሁሉ በመወረሱ የካህናቱ አገልግሎት ፈተና አጋጥሞታል፡፡ ስለዚህ መውጫ መንገድ ነው የተባለው የሰበካ ጉባኤ አደረጃጀት እንደ አንድ መፍትሔ የደረሰላት ቢሆንም አሁንም ግን በሚፈ ለገው ደረጃ አገልግሎቷን መደገፍ የሚያስችል በቂ ገቢ ባለመኖሩ ችግሩ እንዳለ ነው፡፡

ከዚሁ ጋር ተያይዞ የበለጠ እየተጎዱ ያሉት ደግሞ የገጠር አብያተ ክርስቲ ያናት ናቸው፡፡ ቤተክርስቲያን የምትሰ በስበውን ገንዘብ አሰባሰብና ሥርጭቱ አጠቃቀሙ የገንዘብ አስተዳደር ሥርዓቱ መሻሻል ያለበት ቢሆንም ባለው ደረጃም ቢሆን በችግር ላይ ያሉ አጥቢያዎች መኖራቸው ይታወቃል፡፡ እነዚህ ችግረኛ ገዳማትና አድባራት የሚያስፈልጋቸውን ገቢ ለማግኘት በዓመታዊ በዓላት ከምእመናን የሚያገኙት ገቢ ብቻውን በቂ ባለመሆኑ ልመና ለማድረግ እየተገደዱ ቆይተዋል፡፡ ልመናውንም በተለያዩ አጥቢያዎች በማድረግ የተወሰነ ገቢ አግኝቶ አገልግሎታቸውን ለማስቀጠል እየተንገዳገዱ ነው፡፡

 

ይሔ በእንዲህ እያለ በተቸገሩ አብያተ ክርስቲያናት ስም በጎዳና ላይ ልመና የማድረግ አካሔድ እየሰፋና እያደገ መምጣቱ ይታያል፡፡ ይሔ አካሔድ እጅግ አደገኛና የቤተክርስቲያንንም ገጽታ እየጎዳ ያለ ሕገወጥ አካሔድ ነው፡፡

በቤተክርስቲያን ስም የሚፈጸም የጎዳና ላይ ልመና ገጽታ ሲገመገም አብዛኛው ስምሪት በአዲስ አበባና በሌሎች ዋና ዋና ከተሞች የሚደረግ ነው፡፡ የሚደረጉት የጎዳና ላይ ልመናዎች በዓላት በሆኑ ጊዜያትም ከበዓላትም ውጪ የሚደረጉ ናቸው፡፡ የሚደረጉት ልመናዎች ከአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ውጪ በተገኙ ተገቢ ባልሆኑ ጎዳናዎች ላይ ነው፡፡ የሚደረጉትን የጎዳና ላይ ልመናዎች የሚያከናውኑት ካህናት የሚመመስሉም የማይመስሉም ሰዎች ናቸው፡፡ ልመናዎቹ የሚደረጉት በቡድን ወይም በተናጠል ነው፡፡ የጎዳና ላይ ልመናዎች ሲፈፀሙ ጥላ ተዘርግቶ የቅዱሳን ሥዕላት ተይዘው ነው፡፡ እነዚህ ቅዱሳት ሥዕላት በክብር የተያዙ ያልተያዙም ናቸው፡፡

 

የጎዳና ላይ ልመናዎች ሕገ ወጥነት

የጎዳና ላይ ልመናዎች ሕገ ወጥ የሚሆኑባቸው ብዙ ምክንያቶች አሉ፡፡

1/ የቤተ ክርስቲያኒቱን ፈቃድ ያልያዙ የጎዳና ላይ ለማኞች


በቅዱሳን እና በአብያተክርስቲያናት ስም የሚለምኑ የተወሰኑ ግለሰቦችና ቡድኖች ሁሉም ሕጋዊ የቤተክርስቲያኒቱ ፈቃድ የሌላቸው ናቸው፡፡ እነዚህ ወገኖች ከአጥቢያ ቤተክርስቲያናቸው፣ ከወረዳ ቤተክህነት፣ ከሀገረ ስብከት፣ ከጠቅላይ ቤተክህነት የተጻፈ ምንም የፈቃድ ደብዳቤ ሳይዙ በሕገ ወጥነት በማጭበርበር የሚሰ ለፉም ናቸው፡፡ እነዚህ አካላት የራሳቸውን የግል ወይም የቡድን ጥቅም ለማርካት ወይም የቤተክርስቲያንን ስም ለማጉደፍ በድፍረት የተሰለፉ ናቸው፡፡
እነዚህ ወገኖች ምእመናን የቅዱሳን ስም ሲጠራ ራርተው ይሰጣሉ በሚል እምነት በድፍረት ገንዘባቸውን ለመሰ ብሰብ የሚሹ ናቸው፡፡ በዚህ ምክንያት የትኛውም ሕግ በማይደግፋቸው አግባብ በማን አለብኝነት የዋሕ ወገኖችን እያታ ለሉ ያሉ ናቸው፡፡

2/ የተጭበረበሩ ደብዳቤዎች የያዙ የጎዳና ላይ ልመናዎች

አንዳንዶች ደግሞ ሕጋዊ ለማኝ ለመምሰል ከአጥቢያ የተጻፉ የሚመስሉ ከጠቅላይ ቤተክህነት የተጻፉ በሚመስሉ ደብዳቤዎችን በጎዳና ላይ ደርድረው የሚለምኑ ናቸው፡፡ እነዚህ ደብዳቤዎች ሕጋዊ ማኅተም የሌላቸው ወይም ማኅተምን ቢኖራቸውም በማጭበርበር በማስመሰል የተዘጋጁ ወይም ከዚህ ቀደም ተጽፈው ቀንና ቁጥራቸው ላይ ለውጥ በማድረግ አመሳስለው የሚይዟቸው ናቸው፡፡ በዚህም ምክንያት ሕገ ወጥ ናቸው፡፡

3/ በመመሳጠር የተዘጋጁ ደብዳቤዎችን መጠቀም

በአንዳንድ አጥቢያዎች ያሉ የሰበካ ጉባኤ ሓላፊዎች ወይም ሰነዶችን ሕጋዊ የማድረግ ዕድል ያላቸው ግለሰቦች ከአጠቃላዩ የሰበካ ጉባኤ፣ ከማኅበረ ካህናቱና ከምእመናን ስምምነት ሳይደ ረስባቸው ቤተክርስቲያኑ በጎዳና ላይ እንዲለምኑለት ለተወሰኑ በስም ለተጠቀሱ ግለሰቦች ፈቃድ የሰጠ በማስ መሰል በሚወጡ ደብዳቤዎች የሚፈጸሙ የጎዳና ላይ ልመናዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ደብዳቤዎችን ይዞ አንድ መርማሪ በአጥቢያው ያሉ የሁሉንም የሰበካ ጉባኤ አባላት ወይም የልማት ኮሚቴ ዎች ስምምነት ያገኘ ወይም ያላገኘ ስለመሆኑ ማስረጃ ቢፈልግ በቀላሉ እንዲህ መሰል ደብዳቤዎች የሚወጡበትን የሙስና መንገድ ሊደርስበት ይችላል፡፡

4/ ከያዟቸው ደብዳቤዎች የፈቃድ ሐሳብ በወጣ መልኩ ልመና ማድረግ

ከየትኛውም የቤተክህነት አካል በሕጋ ዊነት የሚወጡ ደብዳቤዎች የቤተ ክርስቲያን አገልግሎትን የሚፈጽሙ ወገኖች የቤተክርስቲያንን ወይም የቅዱሳንን ስም እየጠሩ ሥዕል ይዘው በጎዳና ላይ እንዲለምኑ ፈቃድ አይሰጥም፡፡ በአብዛኞቹ የምእመናን ድጋፍ እንዲጠይቁ ፈቃድ የሚሰጣቸው አገልጋዮች ከአጥቢያ ቤተክርስቲያን ውጪ እንዲህ ባለ ግብር እንዲገኙ አያዝም፡፡ አብዛኞቹ በተለይም ከጠቅላይ ቤተክህነት የተጻፉ ደብዳቤዎችን ስናይ ልመና እንዲፈጸም የሚያዙት ልመናው ከሚደረግበት አጥቢያ ጋር በመነጋገርና በመስማማት በዚያው በአጥቢያው ውስጥ ነው፡፡ ስለዚህ ከአጥቢያ ውጪ የሚለምኑ ወገኖች ከያዙት የፈቃድ ደብዳቤ ሐሳብ ውጪ የሚራመዱ ከሆነ ሕገ ወጥ መሆናቸው አይቀሬ ነው፡፡

5/ ገንዘብ መቀበያ ደረሰኝ የሌላቸው የጎዳና ላይ ለማኞች

በጎዳና ላይ የሚለምኑ ሁሉም ማለት ይቻላል ግለሰቦችና ቡድኖች በየትኛውም መጠን ለሚቀርብላቸው ምጽዋት የሚቀ በሉበት ሕጋዊ ደረሰኝ የላቸውም፡፡ ስለዚህ በአድባራትና በገዳማት የሚለምኑት ወገኖች የሰበሰቡት የገንዘብ መጠን ሊታወቅ አይችልም ማለት ነው፡፡ በእርግጠኝነት መናገር የሚቻለው ግን ቤተክርስቲያን እውነተኛ ፈቃድ ስትሰጥ በሕጋዊ ደረሰኝ እንዲሰበሰብ እንጂ ከዚያ በመለስ ምንም ያህል መጠን ያለው ገንዘብ ከምእመናን ቢሰበሰብ ለተለመነለት አጥቢያ በተሰበሰበው መጠን መድረሱን ወይም አለመድረሱን ከዚያም አልፎ የግለሰቦቹ መጠቀሚያ ሆኖ ቀርቶም እንደሆነ በውል ማወቅ አያስችልም፡፡

የዚህ ችግር መንሥኤ ምንድ ነው?

1/ የቤተክርስቲያን ቁጥጥር ልል መሆን


ቤተክርስቲያናችን የራሷ አካል በሆኑ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ስም የሚፈጸሙ ይሔን መሰል የማጭበርበር ድርጊቶች ለመቆጣጠር የዘረጋችው ጊዜያዊ ወይም ቋሚ አሠራር የለም፡፡ ቢኖርም በንቃት አልተንቀሳቀሰም፡፡ ችግሩን በቀላሉ መቅጨት የሚቻል ቢሆንም እየተባበሰ መሔዱ የአሠራር ድክመቱን ያሳያል፡፡ ቤተክርስቲያን ይሔንን ችግር መቆጣጠር የሚኖርባት ለቤተክርስ ቲያኒቱ ክብር ብቻ ሳይሆን በቤተክር ስቲያን ስም የሕዝብ ገንዘብ በግለሰቦች እየተመዘበረ በመምጣቱም ጭምር ነው፡፡ በሌላም በኩል ክርስቲያኖች ቤተክርስቲያንን ለመደገፍ የሚሔዱ በትን ፈቃድ በየጎዳናው በመጥለፍ በቤተ ክርስቲያን ተገኝተው ጸሎት አድርሰው ተባርከው መባቸውን በሥርዓት አስገ ብተው እንዳይሔዱ የሚያደርግ ልማድ ፈጥሯል፡፡ ቤተክርስቲያን በየጎዳናው ላይ ሁሉ እንዳለች እያሰቡ በኪሳቸው ያለውን ገንዘብ እየሰጡ እንዲያልፉ ሆነዋል፡፡ ስለዚህ የዚህ ሁሉ ተጎጂ ራሷ ቤተ ክርስቲያን መሆኗን አውቆ ልል የሆነውን የቁጥጥር ሥርዓት ጠበቅ ማድረግ፣ ምክር መስጠት፣ ካልሆነም ከሕግ አስከባ ሪዎች ጋር በመተባበርም እርምጃ እንዲወሰድ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡

2/ ሙስና

ቤተክርስቲያን እንዲህ መሰል ጥፋቶች በስሟ የሚበቅሉት የግልጽና ስውር የሙስና አሠራሮች በመኖራቸው ነው፡፡ የጎዳና ላይ ልመናዎች እንዲከናወኑ ሕጋዊ ሽፋን ለመስጠት የተሰለፉ በየደረጃው ያሉ የቤተክርስቲያን አስተዳደር ሹማም ንትም እንዳሉ ይጠረጠራሉ፡፡ ለአንድ ቤተክርስቲያን የሚለመንበት በቂ ምክንያት ሳይኖር ወይም ለአንድ ለተወሰነ ጊዜ ችግር የሆነን ነገር ሁሌ እንዳለ በማስመሰል ፈቃድ በመስጠት እንዲለመን የሚያደርጉ ወገኖች አሉ፡፡ ለዚህም ማሳያ የሚሆነው አንዳንድ አብያተ ክርስቲያናት ሕንፃ ቤተክርስቲያን በማሠራት ስም ፕሮጀክቱን በማራዘም ለረጅም ጊዜ እንዲለመንበት በማድረግ ወይም ካለቀም በኋላ ያለ በማስመሰል ልመናዎች እንዲ ቀጥሉ የማድረግ አሠራር አለ፡፡ በዚህም ቢያንስ ዘረፋ ወይም ጥቅማ ጥቅም ለማግኘት የሚሠሩ ወገኖች አሉ፡፡

3/ ሕዝበ ክርስቲያኑ በየዋህነት በማመን መመጽወቱ

ክርስቲያኖች ለለመነ፣ ለጠየቀ መስጠት አግባብና ክርስቲያናዊ ሥነምግባር መሆኑን ስለሚያምኑ በቅዱሳን ስም ተጠርቶ የቅዱሳን ሥዕል ተይዞ ሲለመን ማለፍ ይከብዳቸዋል፡፡ ሌላው ቀርቶ እንዲለምኑበት የተሰጣቸውን የፈቃድ ወረቀት ሐሳብ ወይም የሚቀበሉበትን ሕጋዊ ደረሰኝ የማይጠይቁ ብዙዎች ናቸው፡፡ በሌላም በኩል ለሚሰጡት ሽርፍራፊ ሳንቲም ደረሰኝ መጠየቅ አስፈላጊ ነው ብለው አያምኑም፡፡ ስለዚህም ለእነዚህ ሕገወጥ የጎዳና ላይ ልመናዎች መበራከት የምእመናንንም ድርሻ አለበት፡፡

በእርግጥ አንዳንድ ክርስቲያኖች የተጎዱ አብያተ ክርስቲያናትን ለመርዳት በሚያ ስችል መልክ ተሰባስበው ቀጣይነት ያለው ሕጋዊነትና ሥርዓት ያለው ድጋፍ ችግረኛ ለሆኑ አብያተ ክርስቲ ያናት መስጠት በመጀመራቸው የችግሩ ስፋት የሚቀንስበት ዕድል ሊኖር ይችላል፡፡ የሆነ ሆኖ ግን ምእመናን የጎዳና ላይ ልመና የቤተክርስቲያንን የሃይማኖ ታቸውን ገጽታ የሚያበላሽና ሥርዓት ያጣ ስርቆትንም የሚያባብስ መሆኑን ተረድተው ከዚህ መቆጠብ ካልቻሉ ገንዘባ ቸውን አነሰም በዛም በግልም ይሁን በቡድን ለቤተክርስቲያን በሕጋዊ መንገድ ገቢ ማድረግ እስካልቻሉ ድረስ ችግሩ መቀጠሉ የማይቀር ይሆናል፡፡

limena1የጎዳና ላይ ልመና የሚያስከትለው ችግር

1/ የቤተ ክርስቲያንን ገጽታ ማጥፋቱ

ይህቺ ቅድስትና በቸር ጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ደም የተመሠረተች ቤተክር ስቲያን ክብር ያላት ናት፡፡ ለብዙዎች የእግዚአብሔርን ጸጋ የምታሰጥ ባዕለጸጋ ቤተክርስቲያን ነች፡፡ ‹‹እናንተን እንጂ ያላችሁን አልፈልግም›› እያለች ስታስ ተምር የኖረች ቤተክርስቲያን ነች፡፡ ለምስኪኖች፣ ለተቸገሩ፣ ለደሀ አደጎች ለእጓለ ማውታ ሁሉ የምትደርስ ቤተ ክርስቲያን ነች፡፡ ‹‹ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብፁዕ ነው›› እያለች የምታሰተምር ቤተክርስቲያን ነች፡፡

 

ቤተክርስቲያን ከምእመናን ዐሥራት በኩራታቸውን ተቀብላ የእግዚአብሔርን ገንዘብ የምታስተዳድር እንጂ ዋነኛ ተግባሯ ሙዳየ ምጽዋት መሰብሰብ አይደለም፡፡ ስብከተ ወንጌልን የማንገሥ እንጂ ማዕድን የማገልገል ፍላጎት ያላት አይደለችም፡፡ ማድረግ ሲገባት ደግሞ በሥርዓትና በታማኝነት የምትፈጽምበት አሠራር አላት፡፡

 

የጎዳና ላይ ልመናዎች ግን የቤተ ክርስቲያን መገለጫ ሆነው ተስለዋል፡፡ ማንም ጥላ ይዞ የሚለምን፣ ሥዕል ያንጠለጠለ፣ እጁን የዘረጋ ሁሉ የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን መገለጫ እየሆነ ነው፡፡ ሌሎች ዐበይት ቤተክርስቲያናዊ ተግባራትን ባከናወንን መጠን ክርስቲ ያኖች ሳይጠይቁ የሚያደርጉትን ነገር እኛ ግን ዐበይት ተግባሮቻችንን ቸል ብለን የጎዳና ላይ ልመና ዋነኛ የሥራ ሂደታችን ያደረግነው ያስመስላል፡፡

 

ስለዚህ ነው ቤተክርስቲያናችን የጎዳና ላይ ልመናዎችና መሰል ተገቢ ያልሆኑ ተግባራት ለቤተክርስቲያኒቱ ታሪካዊነት የአርአያነት ሚና የታማኝነት ደረጃ ወዘተን የሚያኮስሱ ይሆናሉ፡፡

2/ የቅዱሳንን ክብር የሚነካ ይሆናል


ቅዱሳንን እግዚአብሔር ያከበራቸው ናቸው፡፡ ሰዎች ክብርን የሚሰጧቸው ወይም የሚቀንሱባቸው አይደሉም፡፡ እነርሱን በማክበር ግን ቤተክርስቲያንና ልጆቿ በረከት ያገኛሉ፤ እግዚአብሔርን ደስ ያሰኛሉ፡፡

ነገር ግን በጎዳና ላይ ልመናዎች የምናየው ነገር የቅዱሳን መላእክትን የቅዱሳን ሰዎችን ስም ጠርተው ሥዕል ይዘው የሚለምኑ ወገኖች በተለያዩ አካሔዶቻቸው ቅዱሳንን ያዋርዳሉ፡፡ በስማቸው ሕገ ወጥ ሥራ የስርቆት ተግባር መፈጸማቸው ጽርፈት ነው፡፡ ንዋየ ቅድሳት ከሥርዓት ውጪ በተያዙ መጠን ይጉላላሉ፡፡ ሥዕሎ ቻቸውን ይዘው አጓጉል ቦታዎች ቆመው መታየታቸው ጽርፈት ነው፡፡ ለቅዱሳት ሥዕላት ክብር በሚነፍግ መልኩ በአያያዝ የተጎዱ በሥርዓት ያልተሠሩ ፀሐይና ዝናብ የተፈራረቀባቸው ሥዕላትን ይዞ መቆም ለሃይማኖት ቤተሰቡም ሆነ ለሚከበሩት ቅዱሳን ክብር አለመስጠት ነው፡፡

3/ የክህነትን ክብር የሚነካ ነው

ብዙ ጊዜ በጎዳና ልመና ላይ የተሰማሩ ግለሰቦችና ቡድኖች ካህናት የሆኑም ያልሆኑም ወገኖች ናቸው፡፡ ነገር ግን አርአያ ክህነትን ተላብሰው ስለሚታዩ ሁልጊዜም በጎዳና ላይ ልመና የሚታዩት ካህናት ናቸው ብሎ ሰዎች እንዲያምኑ እያደረገ ነው፡፡ ካህናት የቤተክርስቲያን መልክና ምልክቶች ናቸው፡፡ በእነርሱ ውስጥ የምትከብረው ወይም ገጽታዋ የሚደበዝዘው የቤተክርስቲያን ነው፡፡ የመላው ካህናት ገጽታ ነው፡፡ ካህናትን ዘወትር የሚሰጡ ሳይሆን የሚቀበሉ፣ የሚመጸውቱ ሳይሆን የሚመጸወቱ አስመስሎ ያቀርባል፡፡ ከዚያም አልፎ በክህነት የሚፈጸመው ዋነኛ ተግባር ልመና እንደሆነ አድርገው በክህነት የሚያምኑም ሆነ የማያምኑ ወገኖች እንዲያስቡ ያደርጋቸዋል፡፡

4/ የሀገርን ገጽታ ይጎዳል


ቤተክርስቲያን በሙዳየ ምጽዋት የምእ መናንን የለጋስነት ስጦታ መሰብሰቧ፣ ዐሥራት በኩራትን መሰብሰቧ በሃይማኖቱ ሕግና ሥርዓት የታወቀ መንፈሳዊ ተግባሯ ነው፡፡ ስለዚህ የትኛውም ተመልካች ቤተክርስቲያን በአጥቢያዋ ካሉ ምእመናን ዐሥራት በኩራት ምጽዋትን ሰበሰበች ብሎ የሚነቅፋት አይኖርም፡፡ ነገር ግን በተገቢው መልኩ በተገቢው ቦታና በሕጋዊ መልክ ካልሆነ ይነቅፋል፡፡

 

የጎዳና ላይ ልመና ግን ከቤተክርስቲያን አልፎ ለሀገርም ገጽታን የሚያጎድፍ በሀገር ውስጥና በውጪ ሀገር ጎብኚዎችም ዘንድ ደስ የማያሰኝ በመሆኑ ለሀገራችን አይጠቅምም፡፡ ሀገር ልመናን በመቀነስ ሥራና ሠራተኛነትን ለማስፋፋት ጥረት ማድረግ የሚገባትም ለሰሚና ተመልካች ሳቢ ሁኔታን ለመፍጠር ነው፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ግን ከአጥቢያ ቤተክር ስቲያን ግቢ ውጪ ወጥቶ ከዕለታዊ ችግራቸው የተነሣ ሕዝብ ባለበት ዐደባባይ ከሚለምኑ ነዳያን ጎን ተሰልፎ ከአማ ኙም ከኢአማኒውም ለቤተክርስቲያን ንዋየ ቅድሳት መግዣ፣ ለሕንፃዋ ማሠሪያ ገንዘብ ለመለመን መሞከር ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለው ነው፡፡

 

5/ የአጥቢያና የሀገረ ስብከቶችን ክብር ይነካል

 

የሚለመንላቸው አጥቢያዎች ስማቸው አለአግባብ በየጎዳናው ለረጅም ጊዜ መነሣቱ ክብር አይሆንላቸውም፡፡ በስማቸው ሕገ ወጥ ተግባር ሲከናወን ሲታይ አጥቢ ያውን ለሚያውቁ ምእመናንና ካህናት የሚያምም ይሆናል፡፡ ለአጥቢያው ብቻ ሳይሆን በዚህ ሀገረ ስብከት በዚህ ወረዳ ለሚገኘው ተብሎ ስለሚለመን ለዚያ ሁሉ ወገን የሚያምም ይሆናል፡፡

6/ ሥራ ፈትነትን ያበረታታል

ቤተክርስቲያን ያላት ትምህርት ‹‹ሊሠራ የማይወድ አይብላ›› የሚል ነው፡፡ ነገር ግን ሕገ ወጥ የጎዳና ላይ ልመናዎች በአቋራጭ መክበርን ያለሥራ ያለድካም መጠቀምን የሚያመጡ ናቸው፡፡ በመሆኑም ጉዳቱ ለዜጎች ሁሉ ነው፡፡ የሚሠራውን ተስፋ የሚያስቆርጥና ተመሳሳይ የአቋራጭ መንገዶችን እየፈለገ ምርታማ ባልሆኑ ሥራዎች በመሰማራት ከዚያም አልፎ በሥራ ፈትነት በሕገ ወጥ ተግባራት ውስጥ እንዲገባ ያበረታታሉ፡፡ የቤተክርስቲያንን አርአ ያነትም ያጎድፋል፡፡

7/ ለቤተ ክርስቲያን ቤተሰቦች ያሳፍራል

ቤተ ክርስቲያንና ቤተሰቦቿ ከሥራ ይልቅ ልመናን የሚመርጡ ስለሚያስ መስል በሌሎች ወገኖች በሚደርስብን ትችት ምእመናን ይሸማቀቃሉ፡፡ ምእመናን የሚፈለገውን ያህል በማይ ወስኑባት በማይመክሩባት ቤተክርስቲያን ውስጥ ይሔ መሆኑ ደግሞ ምእመናንን የሚያስቆጣበት ደረጃ ላይ ያደርሳል፡፡ ካህናት አመኔታ እንዲያጡ በር ይከፍታል፡፡

8/ ምእመናንን ያዘናጋል

ምእመናን ምጽዋትና ዐሥራት በኩራትን ለይተው ማድረግ እንደሚገባቸው በውል ትምህርት በበቂ ባልተሰጠበት ሁኔታ ውስጥ እንዲህ ያሉ ሕገ ወጥ የጎዳና ላይ ልመናዎች ሲበራከቱ የዋህ ምእመናን ቤተክርስቲያንን ያገኙ ስለሚመስላቸው ዐሥራት በኩራታቸውን በአግባቡ ለማውጣት ይቸገራሉ፡፡ በጥቂቱ በመርካት ከአጥቢያ ቤተክርስቲያን በአፍአ ይቀራሉ፡፡ ምጽዋታቸውንም በአግባቡ ሊሰጡ የሚችሉበት ዕድል አይኖራቸውም፡፡

9/ ሌሎች ችግሮች

የጎዳና ላይ ልመናዎች የሚያስከትሉት ሌላው ጉዳት ከሚለምኑት ሰዎች ማንነትና ተግባር ጋር በተያያዘ የሚያስ ከትለው ችግር ነው፡፡ በልመና ላይ የዋሉ ሰዎች የውሏቸው መጨረሻ የት ነው? የት ያመሻሉ? የት ያድራሉ? ከእነማን ጋር ይውላሉ? የሚለው ሌላው አሳሳቢ ነገር ነው፡፡ ያለደረሰኝ በሕገ ወጥ መልክ የተሰበሰበውን ገንዘብ ይዘው በየመጠጥ ቤቶች ተሰይመው የሚያመሹ በርካቶች ናቸው፡፡ ተደራ ጅተው፣ ማደሪያ ተከራይተው በዓላት ባሉበት የአዲስ አበባ ጎዳናዎች ሁሉ ቆመው ውለው ማታ ተሰባስበው ያገኙትን ገንዘብ ተካፍለው የሚበተኑ ቡድኖች አሉ፡፡ የቡድኖቹ አስተባባሪዎችም አሉ፡፡ ያዘጋጁትን የፈቃድ ደብዳቤ የሚመስል ማጭበርበሪያ ይዘው የሚለምኑ ሰዎችን አደራጅተው ደብዳቤውን ፎቶ ኮፒ አድርገው የሚያሰማሩ ከዚያም ከየለማኞቹ የድርሻቸውን ተቀብለው ለቀጣዩ ዙር ልመና ተቀጣጥረው የሚበታተኑ ሁሉ አሉ፡፡ ይህ ሁሉ የሚፈጸመው በቤተክር ስቲያኒቱ ስም መሆኑ ሲታሰብ የሚያሳዝን ነው፡፡

 

ሌላው አሳሳቢው ነገር በየቦታው በሚታዩ ልመናዎች የሚያስተባብሩት ወይም የሚለምኑት ሰዎች ተጠሪነታቸው ለጥቂትና ተመሳሳይ ሰዎች የመሆኑ ነገር ነው፡፡ እነዚህ ግለሰቦች የፈቃድ ደብዳቤ ብለው በሚይዙት ላይ በልዩ ልዩ ሥፍራዎች ያሉ ሰዎች በያዟቸው የፈቃድ ደብዳቤዎች ላይ በአንድም በሌላ መንገድ ተጠቅሰዋል፡፡ እነዚህ ግለሰቦች በተለይም የአዲስ አበባን የጎዳና ላይ ልመናዎች ገዢ ሆነው የተቀመጡ ሰዎች ናቸው፡፡ ምናልባትም ሕጋዊ መልክ እንዲኖራቸው ከቤተክህነቱ አንዳንድ ግለሰቦች ጋር የጥቅም ግንኙነት ያላቸውም ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ስለዚህ የሚለምኑት ከሚያስለምኑ ሕጋዊ ነን ከሚሉ ገዢዎቻቸው ጋር ተቀናጅተው የሚፈጽሙት ጥፋት ነው፡፡

 

ሌላው አሳሳቢው ነገር የሀገሪቱን ሕግ የሚያስከብሩ ደንብ አስከባሪዎችና ፖሊስ ቤተክርስቲያንን እና ክርስቲያኑን ማኅበረሰብ በመፍራት ለመጠየቅ የሚደፍ ሯቸው አለመሆናቸው ነው፡፡ በፊታቸው የሚዘረጓቸውን ማስፈራሪያ ወረቀቶች አይተው ወይም የሚሰጣቸውን መጽዋች ፈርተው ወይም አይመለከተንም በማለት ወዘተ የሕግ አስከባሪዎች ስለሚያልፏቸው ጠያቂ እንደሌላቸው በማሰብ እነዚህ በቤተክርስቲያን ስም በመለመን የብዙዎችን ገንዘብ አለአግባብ እየዘረፉ ይገኛሉ፡፡

መፍትሔ

ቤተክርስቲያን በስሟ የሚፈጸሙ ልመናዎችን ለማስቆም መትጋት ያለባት አሁን ነው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ሙስናን ከቤተክርስቲያን ለማጥፋት እሠራለሁ ብሎ እየተጋ ባለበት በዚህ ዘመን ከእነዚህ ጥቃቅን ቀበሮዎች ጀምሮ ወደ ታላላቆቹ መገስገስ ይገባዋል፡፡ ታላላቆቹ ሙሰኞች በእነዚህ ጥቃቅን መሠረቶች ላይ የቆሙ ናቸው፡፡

 

ቤተክርስቲያን እንዲህ ያሉ ሕገ ወጦችን ማጥፋት የሚገባት የቅድስና ባለቤት በሆነችው ቤተክርስቲያን ስም የሚፈጸም የስርቆት ተግባር ኃጢአት በመሆኑ ነው፡፡ ስለዚህ በልመና ላይ የተሰማሩትን ጨምሮ በዚሁ የጥፋት መንገድ ለመሳተፍ እየተንደረደሩ ያሉትን ለመታደግ ይረዳታል፡፡ በሌላ መልኩ ምእመናን ገንዘባቸውን በቤተክርስቲያን ስም እንዳይዘረፉ ከመጠበቅ አንጻር ነው፡፡ በሌላ መልኩ ደግሞ የቤተክርስቲያንን ገጽታ እንዳይጎድፍ ከመጠበቅ አንጻር ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በቤተክርስቲያኒቱ መሠልጠን ያለበት ሕጋዊ አሠራር ብቻ መሆኑን አስረግጦ ለማስረዳት ለማሳየት ይጠቅማል፡፡

 

ስለዚህም በቅድሚያ በቤተክርስቲያን ስም በጎዳና ላይ መለመን ከብዙ ነገሮች አንጻር ምን ያህል አግባብ ነው የሚለውን በውል በማጤን ግልጽ አቋም መያዝ ከቤተክርስቲያን ይጠበቃል፡፡ ከዚህ አስከትሎም አሁን በጎዳና ላይ እየተፈጸሙ ያሉ ልመናዎችን ሕጋዊነት መመርመር ያስፈልጋል፡፡ ለጎዳና ላይ ልመናዎች ፈቃድ የሚሰጠው ማን ነው? ፈቃዱን ለእነማን ሰጠ? ለምን ዓላማ ሰጠ? ተግባሩ ፈቃድ በተሰጠበት አግባብ ተፈጽሟል? ፈቃዱ እስከ መቼ የሚሠራ ነው? በፈቃዱ የተሰበሰበው ገንዘብ ለታሰበው ዓላማ እየዋለ ነው? በትክክል የፈቃድ ደብዳቤው ወጣ ከተባለበት መዝገብ ቤት ወጥቷል? ወዘተ የሚሉ ጥያቄዎችን አንሥቶ የቤተክርስቲያኒቱ ታማኝ የሕግ አስከባሪ አካላት ከተለያዩ የሚመለከታቸው አካላት ጋር መመርመርና እርምጃ ማስወሰድ አለባቸው፡፡

ከቤተክርስቲያን አስተዳደር ሌላ ግን ከመንግሥት አካላት ጋር ተባብሮ ቢያንስ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶችና ሌሎች ቁጭቱ ያላቸው አገልጋዮችም የእነዚህን የጎዳና ላይ ልመናዎች ለማስቀረትና የቤተክርስቲያናችንን ክብር ማስጠበቅ አለብን፡፡

መሰናክል ያለበትን ገንዘብ የሚሰበስብ ሰው ገንዘብ በመሰብሰቡ ኃጢአት አድርጓልና እንዳይሰበስብ ይገባዋል/ፍት.ነገ. አንቀ.16 ቁ.648/

ዳግመኛም ገንዘብ እያለው ምጽዋት ለሚቀበል ሰው ወዮለት አለ፤ ራሱን መርዳት እየተቻለው ከሌሎች መቀበልን የሚወድ ሰው ወዮለት እንዲህ ያለውን ግን በፍርድ ቀን እግዚአብሔር ይመረምረውል››/ፍት.ነገ.አንቀ.16 ቁ.634/

ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት፤21ኛ ዓመት ቁጥር 7፤ ኅዳር 2006 ዓ.ም.

 

ዘመነ አስተርእዮ

 ጥር 21 ቀን 2006 ዓ.ም.

 

ር/ደብር ብርሃኑ አካል

አስተርእዮ ቃሉ የግእዝ ቃል ሲሆን መታየት መገለጥ ማለት ነው፡፡ ገሐድ የሚለው ቃልም በጾምነቱ ሌላ ትንታኔ ሲኖረው ትርጉሙ ያው መገለጥ ማለት ነው፡፡ በግሪክ ኤጲፋኒ ይሉታል፡፡ የኛም ሊቃውንት ቀጥታ በመውሰድ ኤጲፋኒያ እያሉ በዜማ መጻሕፍቶቻቸው ይጠሩታል፡፡ ትርጉሙም ከላይ ከጠቀስናቸው ጋር አንድ ነው፡፡

አስተርአየ የተባለው ግሥ ራሱን ችሎ ሳይለወጥ በአምስቱ አዕማድ የሚፈታ ብቸኛ ግሥ ነው፡፡ ይህም ማለት፡- አስተርአየ፤ ታየ፤ ተያየ፤ አሳየ፤ አስተያየ፤ አየ ተብሎ ይፈታል ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ዘመነ አስተርእዮ ሲያጥር ከጥር 11 ቀን እስከ ጥር 30 ቀን ይሆናል፡፡ በዚህም መሠረት 20 ቀናት ይሆናሉ፡፡ ሲረዝም ደግሞ ከጥር 11 ቀን እስከ መጋቢት 3 ቀን ይሆናል፡፡ ይህም 53 ቀናት ይሆናሉ ማለት ነው፡፡

 

ጌታን ለሐዋርያት ህፅበተ እግር ያደረገበት ቀንም ከጸሎተ ሐሙስ እስከ ጰራቅሊጦስ ቢቆጠር 53 ቀናት ስለሚሆኑ የእነዚህ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ዮሐንስ በጥምቀት ዕለት ለልዕልና /ጌታ ሰውን ምን ያህል እንዳከበረው/ ለማሳየት እጁን ከጌታ ራስ በላይ ከፍ እንዳደረገ ጌታም ለትህትና እጁን ከሐዋርያት እግር በታች ዝቅ አድርጎ እግራቸውን አጥቧቸዋልና ነው፡፡ ጥምቀት የህጽበት አምሳል ሲሆን፤ /ህጽበት/ መታጠብ በንባብ አንድ ሆኖ ሁለት ምሥጢራት አሉት፡፡

አንደኛ፤- ምእመናን የእንግዳ እግር እንዲያጥቡ ትምህርት ማስተማሩ ሲሆን፤ ሁለተኛው ለሐዋርያት ጥምቀት ነው፡፡

በጸሎተ ሐሙስ ቢጠመቁም መንፈስ ቅዱስ የተቀበሉት የጰራቅሊጦስ ነውና ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ፤ ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሳርያን ስለ ቅዱሳን ሐዋርያት ጥምቀት እንደጠየቀውና ጥምቀታቸው ህጽበተ እግር መሆኑን እንደመለሰለት፡፡

 

በሌላ በኩል ከዘመነ ልደት እስከ ጥምቀት ተወልደ፤ ተሰገወ /ሰው ሆነ/ ይባላል እንጂ አስተርአየ አይባልም፡፡ ከጥምቀት በኋላ ግን አብሮ ተባብሮ ተጠምቀ፤ ተወለደ፤ ተሰገወ አስተርአየ ይባላል፡፡ ከጥምቀት በፊት አስተርእዮ ለመባሉ በሦስት ነገሮች ነው፡፡

 

አንደኛ፡- የማይታየው ረቂቅ አምላክ በበረት ተወልዶ፤ በጨርቅ ተጠቅልሎ ቢታይና እንደ ሕፃን ሲያለቅስ ቢሰማም ሰው ሁሉ ሠላሳ ዓመት ሲሞላው ሙሉ ሰው ይሆናል እንደሚባለው፤ አምላክ ነኝ ብሎ በአንድ ቀን ሳያድግ በጥቂቱ ማደጉንና ስደት እንደ ውርደት ሆኖ እንዳይቆጠር ለሰዎች ጀምሮ ለመስጠት፤ ሄሮድስም ሊገድለው ይፈልገው ስለነበር የሚሰደድበት እንጂ የሚታይበት ስላልነበረ ነው፡፡

 

ሁለተኛ፡- ሰው በተፈጥሮም ሆነ በትምህርት አዋቂ ቢሆን ለሚመለከተው ሥራና ደረጃ እስከ ተወሰነ ጊዜ ይህ ሕፃን ለእንዲህ ያለ ማዕረግ ይሆናል አይባልም፡፡ ተንከባክባችሁ አሳድጉት ይባላል እንጂ፤ አዋቂ ነው አይባልም፡፡ ያውቃል ተብሎም ለትልቅ ደረጃ አይበቃም፡፡ በየትኛውም ሓላፊነት ላይ አይሰጥም ራሱን በመግዛት ይጠበቃል እንጂ፡፡ እንዲሁም ጌታ የመንፈሳዊ እና የሥጋዊ ባለሥልጣን ቢሆንም ፍፁም ሰው ሆኗልና የሰውን ሥርዓት ከኃጢአት በቀር ለመፈጸም በበሕቀ ልሕቀ ይላል፡፡ አምላክ ነኝና ሁሉን በዕለቱ ልፈጽም ሳይል በየጥቂቱ ማደጉን እናያለን፡፡ በዚህም የተነሣ ሰው ሁሉ 30 ዓመት ሲሆነው ሕግጋትን እንዲወክል እንዲወስን እስከ 30 ዓመት መታገሡ ስለዚሁ ነው፡፡ ከሠላሳ ዓመት በኋላ ግን ሰው ቢመቸው ይወፍራል፤ ቢከፋው ይከሳል እንጂ ቁመት አይጨምርም አይቀንስም፡፡ ስለዚህ ጌታ ሙሉ ሰው የ30 ዓመት አዕምሮው የተስተካከለለት ሰው /ጎልማሳ ሆኖ በመታየቱ ዘመነ አስተርእዮ ተብሏል፡፡

 

ሦስተኛው፤- በ30 ዓመት እሱ ሊጠመቅበት ሳይሆን የመጀመሪያ መንፈሳዊ ሕግና ሥርዓት መሠረት የሆኑ ጥምቀትንና ጾምን ሰርቶ በመሳየትና መመሪያ አድርጎ በመስጠት አምስት ገበያ ያህል ሰው የቃሉን ትምህርት ለመስማት፤ የእጁን ተአምራት ለማየት፤ እሱ ሙሉ ሰው ሆኖ ተገልጾ ትምህርት፤ ተአምራት የሚያደርግበት ሥራዬ ብሎ የመጣበት መንፈሳዊ ሕግና ሥርዓት የተፈጸመበት ዘመን ነው፡፡

 

የታየውም ብቻ አይደለም፤ አብ ይህ የምወደው ልጄ ነው፤ ሲል መንፈስ ቅዱስም በእርግብ አምሳል ረቂቁ የታየበት የሥላሴ አንድነትና ሦስትነት ምሥጢር የተገለጠበት ስለሆነ ዘመነ አስተርእዮ ተብሏል፡፡

 

በዚህ ምክንያትም ሌሎች በዓሎችም ይጠሩበታል፡፡ ለምሳሌ ድንግል ማርያም ጥር 21 ቀን ነፍሷ ከሥጋዋ ተለይቶ በደመና ተነጥቃ ወደ ገነት በመግባት ለጻድቃን ሰዎችና ለመላእክት በሰማይና በምድር የተሰጣት ጸጋና ክብር የተገለጸበት ዕለት ስለሆነ በዓሉ አስተርእዮ ማርያም ይባላል፡፡ የኢትዮጵያ ሊቃውንት በዚህ ቃል ሐሳባቸውን ያስተባብራሉ፡፡ ቅዱስ ያሬድ አምላክ በሥጋ ከድንግል መወለዱን በዚህ አካለ መጠን ለዓለም መገለጡን አስተርእዮ ብሎ ሲናገር፤ አባ ጽጌ ብርሃን ደግሞ በማኅሌተ ጽጌ “የትንቢት አበባ እግዚአብሔር እኛን ሥጋ የሆነውን የአንቺን ሥጋ ለብሶ በምድር እንደተገለጠ ለእኛም እንዲታወቅ ድንግል ሆይ የወገናችን መመኪያ ዛሬ ለእናታችን ለማርያም በሰማይ ፍጹም በደስታ መገለጥ ሆነ እያልን እናመሰግናለን” ብሏል፡፡ ዳዊትም እንዲህ አለ “በከመ ሰማዕና ከማሁ ርኢነ” መዝ. 47፡6 ፡፡ በነቢያት ይወለዳል ሲባል የሰማነው በበረት ተጥሎ፤ በጨርቅ ተጠቅልሎ በግዕዘ ሕፃናት ሲያለቅስ ሰማነው እንዲሁም በዮርዳኖስ ሲጠመቅ አየነው፡፡

 

የቤተ መጻሕፍቱን የመረጃ ክምችት በዘመናዊ ለማሳደግ ማእከሉ ጥሪ አቀረበ

ጥር 20 ቀን 2006 ዓ.ም.  

በእንዳለ ደምስስ

“ስትመጣ ….መጻሕፍቱን ይልቁንም በብራና የተጻፉትን አምጣልኝ ” 2ኛ ጢሞ4፡13

የማኅበረ ቅዱሳንን ቤተ መጻሕፍት የመረጃ ክምችት ለማሣደግና በዘመናዊ መልኩ ለማደራጀት የ3ኛ ዙር ልዩ የመጻሕፍትና ቤተ መጻሕፍቱን የሚገለግሉ ቁሳቁሶችን ለማሰባሰብ መርሐ ግብር ማዘጋጀቱን የማኅበሩ ጥናትና ምርምር ማእከል ገለጸ፡፡ ከጥር 2 እስከ ጥር 30/ 2006 ዓ.ም የሚቆየው የመጻሕፍትና የቁሳቁስ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብሩ በማኅበረ ቅዱሳን ሕንፃ እና በማኅበሩ የንዋያተ ቅዱሳት መሸጫ ሱቆች ከጧቱ 3፡00 እስከ ምሽቱ 1፡00 ሰዓት ይካሔዳል፡፡

በዚሁ መሠረት ቤተ መጻሕፍቱን ለሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ ለተመራማሪዎች፤ ነገ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ለሚረከቡ ወጣቶችና ተማሪዎች ትልቅ እገዛ ማድረግ የሚችል በመሆኑ፤ መጻሕፍትን በመለገስ በሥጋም በነፍስም ተጠቃሚ የሚሆን ትውልድ ለመፍጠር የበኩልዎን ድርሻ ይወጡ ዘንድ ተጋብዘዋል፡፡

ቤተ መጻሕፍቱ ከ1996ዓ.ም – 1999 ዓ.ም በጎ ሐሳብ ባላቸዉ አገልጋዮች በለገሱት መጻሕፍት፤ በትንሽ ኮንቴነር ውስጥ ለማኅበሩ አገልጋዮች ብቻ የውሰት አገልግሎት በመስጠት የተቋቋመ ሲሆን፤ የመረጃ ሀብቶቹ ከ500 የማይበልጡ ነበሩ፤ ተገልጋዮችም ውስን ነበሩ፡፡

 

ከ2000 ዓ.ም-2003 ዓ.ም ቤተ መጻሕፍቱ በዲ.ዲ.ሲ. /Dewey Decimal Classification/ ሕግ መሠረት በዕውቀት ዘርፍ ተለይተው እንዲደራጁ በማድረግ ግንባታው ባልተጠናቀቀ የማኅበሩ ሕንፃ ውስጥ የንባብ አገልግሎት ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ የመረጃ ሀብት ክምችቱም በዓይነትና በብዛት ጨምሮ 3000 በማድረስ፤ ጥናታዊ ጽሑፎች ተሰብስበዉ ለአገልግሎት ዉለዋል፡፡

 

በዚህ ወቅት ብዙ መጻሕፍትን በስጦታ ለመሰብሰብ የተቻለ ሲሆን ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ ከ 400 በላይ መጻሕፍትን አበርክተዋል፡፡ ከ2004 ዓ.ም – 2006 ዓ.ም ባሉት ዓመታትም፤ የመረጃ ሀብቶች ለአያያዝና ለአጠቃቀም በሚያመች ሁኔታ በማደራጀት በምቹ የአገልግሎት ክፍል ውስጥ የንባብ እና የውሰት አገልግሎት ይሰጣል፡፡ ክምችቱም 5000 የታተመ ቅጅ፤ 5000 ያልታተመ ቅጂ ላይ ደርሷል፡፡ አገልግሎቱ በኮምፒውተር የታገዘ በማድረግ በመካነ ድር እና በሶፍትዌር አገልግሎት ለመስጠት በዝግጅት ላይ ይገኛል፡፡ በቀን በአማካይ ከ50 ለሚበልጡ ሰዎች አገልግሎት ይሰጣል፤ የቤተ መጻሕፍት አገልግሎት ፖሊሲ እና መመሪያም ተዘጋጅቷል፡፡

 

ከ2007 ዓ.ም – 2009 ዓ.ም ድረስ ክምችቱ ወደ 40,000 /አርባ ሺሕ/ በማሳደግ በሶፍትዌር የታገዘና ቀልጣፋ የE-Library፤ የኢንተርኔት እና የዲጂታል አገልግሎት መስጠት የሚያስችለው ተደርጎ እንዲደራጅ የታቀደ ሲሆን፤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለጥናትና ምርምር የሚሆን ማዕከላዊ የመረጃ ተቋም ይሆናል፡፡

 

ምእመናን ሙያዊ አገልግሎት ከመስጠት ጀምሮ የመረጃ ምንጮችን (መጻሕፍት፣መጽሔት፣ ጋዜጦች) እና የቤተ መጻሕፍት መገልገያዎችን (ኮምፒዉተር፣ ስካነር፣ ፎቶ ኮፒ ማሽን፣ ሲዲ፣ ወንበር እና ጠረጴዛ) በመለገስ፤ የቤተ መጻሕፍቱን ደረጃ በማሳደግ ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲሰጥ ለማስቻል አቅማቸው የፈቀደውን ልገሳ እንዲያደርጉ የማኅበሩ ጥናትና ምርምር ማእከል ጥሪ አቅርቧል፡፡

 

bushana

የሆሳዕና ቡሻና በዐታ ለማርያም ገዳም ተቃጠለ

 ጥር 13 ቀን 2006 ዓም.                            

በእንዳለ ደምስስ

በሐድያና ስልጢ ሀገረ ስብከት ጎረጎራ ወረዳ ውቅሮ ፋለታ ቀበሌ የደብረ ምጥማቅ ቡሻና በዓታ ለማርያም ገዳም ጥር 10 ቀን 2006 ዓ.ም. የከተራ ዕለት መነሻው ባልተወቀ ምክንያት ሙሉ ለሙሉ መቃጠሉን የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መልአከ ገነት ቆሞስ አባ ቢኒያም መንቻሮ ገለጹ፡፡bushana

 

ሥራ አስኪያጁ በሰጡን መረጃም የከተራ ዕለት የበዐታ ለማርያም ታቦት ወደ ጥምቀተ ባሕር ከወረደ በኋላ ከምሽቱ 12፡00 ሰዓት ላይ መቃጠሉን ገልጸው ቤተ ክርስቲያኑ ንዋያተ ቅዱሳቱን ጨምሮ ሙሉ ለሙሉ ወድሟል ብለዋል፡፡

 

በካዝና ውሰጥ የነበረው የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጽላት ካዝናው በእሳቱ በከፍተኛ ሁኔታ በመለብለቡ ምክንያት መክፈት እንዳልተቻለና መቃጠልና አለመቃጠሉን እንዳልተረጋገጠ ያስታወቁት ሥራ አስኪያጁ፤ ጉዳዩን ለፖሊስ በማሳወቅ የቃጠሎውን መንስኤ ለማጥራት ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡

 

የቡሻና በዐታ ለማርያም ገዳም ከዚህ በፊት ሥዕለ አድኅኖ በዛፎች ላይ ታይቶበት በነበረ ቦታ መቃኞ ተሰርቶለት ሐምሌ 2001 ዓ.ም. ቅዳሴ ቤቱ እንደተከበረ ይታወቃል፡፡

 

06Begena

ትልቁ በገና

ጥር 11 ቀን 2006 ዓ.ም.                                                                                                                                                        

እንዳለ ደምስስ

የማኅበረ ቅዱሳን የመዝሙር ክፍል አባላትና የአቡነ ጎርጎርዮስ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል በበገና ድርደራ የሠለጠኑ 250 ወጣቶችን የከተራ በዓልን ለማክበር የመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳምን በዝማሬ አጅበው ወደ ጃንሜዳ 06Begenaሰልፋቸውን ይዘው በገናቸውን እየደረደሩ ይጓዛሉ፡፡ አሰላለፋቸውና ብዛታቸው እንዲሁም ጸዓዳ አለባበሳቸው ለዓይን ይማርካሉ፤ እንደ ምንጭ ውኃ ኮለል እያለ የሚፈሰው ዝማሬ ነፍስን ያለመልማል፡፡ ምእመናን በትኩትና በተመስጦ፤ ጎብኚዎች ባዩት ነገር በመገረም የፎቶ ግራፍና የቪዲዮ ካሜራቸውን አነጣጥረው የቻሉትን ያህል ያነሳሉ፡፡

 

በመካከላቸው አንድ በገና ከሁሉም ቁመት በላይ ረዝሞ ይታያል፡፡ ሰልፉ ቆም ሲል ጠጋ ብዬ ተመለከትኩት፡፡ ከዚህ በፊት እንዲህ አይነት ትልቅ በገና አይቼ እንደማላውቅ እርግጠኛ ነኝ፡፡ በገናውን የያዙት ልጆች መገረሜን አስተውለው “ይህ በገና በዓለማችን ከሚገኙ በገናዎች ትልቁ ነው፡፡ በገና እግዚአብሔርን ለማመስገን የምትጠቀመው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርሰቲያን ብቻ ናት፡፡ እስከ ዛሬ ኢትዮጵያ ውስጥም ይህንን በገና በትልቅነቱ የሚስተካከለው የለም” አሉኝ፡፡ በገናውን እንደ ሕፃን ልጅ በፍቅር እንደሚያሻሽ አባት ዳሰስኩት፡፡

 

በገናው ሁለት ሜትር ከሃያ ሳንቲ ሜትር ይረዝማል፡፡ አሥር አውታሮች ሲኖሩት እያንዳንዱ አውታር በስምንት በጎች አንጀት የተሠራ ነው፡፡ አሥሩ አውታሮች በአጠቃላይ በ80 በጎች አንጀት ተዘጋጅተዋል፡፡ ከላይ ያለው ብርኩማ ስልሳ ሳንቲ ሜትር ይረዝማል፡፡ በተጨማሪም በገናውን ለማዘጋጀት የአንድ ትልቅ በሬ ቆዳ ፈጅቷል፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን በየዓመቱ በጥምቀት በዓል ላይ ለታቦታት ክብር ሲባል፤ እንዲሁም ሊጠፋ ተቀርቦ የነበረውን የቤተ ክርስቲያናችን ቅርስ ቀድሞ ወደነበረበት ለመመለስና ለትውልድ ለማስተላለፍ በአቡነ ጎርጎርዮስ ሥልጠና ማእከል ወጣቶችን በማሰልጠን ላይ ይገኛል፡፡

 

06Epiphany17

ለጥምቀት በዓል በክብር የወጡት ታቦታት በክብር ተመልሰዋል

 ጥር 11 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

ለጥምቀት በዓል ከመንበራቸው በክብር የወጡት ታቦታት ወደመጡበት አብያተ ክርስቲያናት በእልልታና በዝማሬ ታጅበው ተመልሰዋል፡፡ከሌሊቱ 12፡30 ሰዓት ጀምሮ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም፤ ወእጨጌ ዘመንበረ 06Epiphany17ተክለ ሃይማኖት ፤ ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ ከሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዩልዮስ፤ ከተለያዩ ሀገራት አምባሳደሮችና የመንግሥት ተወካዮች ጋር በመሆን በጃንሜዳ ጥምቀተ ባሕር ተገኝተዋል፡፡

 06Epiphany21

በቅዱስነታቸው መሪነት የጸሎተ ወንጌል ሥርዓት በማድረስ በዐራቱም ማእዘናት፤ ከዐራቱም የወንጌል ክፍሎች ዕለቱን በማስመልከት ምንባባት ተነበዋል፡፡ ቀጥሎም ቅዱስነታቸው ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር ሆነው ጸበሉን ባርከው  ለምእመናን ረጭተዋል፡፡

 

የጥምቀት ሥነሥርዓቱ ቀጥሎም የወልደ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና የሰንበት ትምህርት ቤቱ መዘምራን ዕለቱን በማስመልከት ያሬዳዊ ዝማሬ አቅርበዋል፡፡06Epiphany22የሕንድ ኦርቶዶክስ ሊቀ ጳጳስ የሆኑት ብፁዕ አቡነ ዩልዮስ ባስላለፉት መልእክት “የሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እኅትማማቾችና የቀረበ ግንኙነት ያላቸው ናቸው፡፡  በተለይም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታላቅ ታሪክና ትውፊት ያላት በመሆኗ የጥምቀት በዓልን በደመቀና ማራኪ በሆነ ሃይማኖታዊ ሥነሥርዓት የምታከብር ብቸኛ ቤተ ክርስቲያን ናት” ብለዋል፡፡

 

 

ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ በመጨረሻ በሰጡት ቃለ ምዕዳን “ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ይቀድስ፤ ያጣነውን ልጅነት ይመልስልን ዘንድ በዮርዳኖስ ወንዝ በዮሐንስ እጅ ተጠመቀ፡፡ ሰላሙንም አደለን፡፡ ይህንንም ጠብቀን መኖር ይገባናል” ብለዋል፡፡

 

በመጨረሻም በትናንትናው ዕለት በክብር ከየአብያተ ክርስቲያናቱ ወጥተው ወደ ጥምቀተ ባሕር የወረዱት ታቦታት በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ በሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራንና ምአመናን ታጅበው ወደየመጡበት በክብር ተመልሰዋል፡፡ የቅዱስ ሚካኤል ታቦታት ግን በነገው እለት የሚመለሱ በመሆኑ በዚያው ይገኛሉ፡፡

 

የጥምቀት በዓል አከባበር በጃን ሜዳ

 ጥር 11 ቀን 2006 ዓ.ም

የከተራ በዓል ጥር 10 ቀን 2006 ዓ.ም. በጃሜዳ ቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በድምቀት ተከብሮ የዋለ ሲሆን፤ ምሽቱን ደግሞ በስብከተ ወንጌልና በዝማሬ ቀጥሎ በሥርዓተ ቅዳሴ ተፈጽሟል፡፡ በመላው ኢትዮጵያ በሚገኙ የጥምቀተ ባሕር ቦታዎችም በተመሳሳይ ሁኔታ የከተራ በዓል በድምቀት ተከብሯል፡፡

ጥር 11 ቀን 2006 ዓ.ም. ከሌሊቱ 12 ሰዓት ጀምሮ ልዩ ልዩ መርሐ ግብሮች እየተካሔዱ ሲሆን፤ ጃን ሜዳ የሚካሔደው ሥነሥርዓት ቅዱስነታቸውና ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በጸሎተ ወንጌል ተጀምሮ የጥምቀት መርሐ ግብሩ ይቀጥላል፡፡ የእለቱ ተረኛ የሆነው የወልደ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ዝማሬ የበዓሉ አካል እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡

 

የከተራ በዓል በደብረ ታቦር ከተማ በድምቀት ተከበረ

 

 

ጥር10 ቀን 2006                                                                                                                      ዳንኤል  አለሙ  ደብረ ታቦር ማእከል

በደብረ ታቦር ከተማ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሰት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶችና ማኅበራት እንዲሁም ሕዝበ ክርስቲያኑ ከሰባት አጥቢያ ቤተ ክርስቲያናት የመጡ ታቦታትን አጅበው በአጅባር ባሕረ ጥምቀት በድምቀት ተከበረ፡፡

የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንቱ ታባታቱን በቃለ እግዚአብሔርና በቅዱስ ያሬድ ዜማ፤ ከሰ/ትቤት መዘምራንና ምእመናን ጋር በምስጋናና በእልልታ በማጀብ በዓሉን አድምቀውታል፡፡

የከተራ በዓል መንፈሳዊ ይዘት በተሞላበት ሁኔታ በነጫጭ አልባሳት በደመቁ ምእመናን እና ምእመናት ተከብሮ ሲውል፤ ለከተማው ህዝብ የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ ባጃጆች በባንዲራ እና ምስጢረ ጥምቀቱን በሚገልፁ ጥቅሶች ተውበው የተለየ ድምቀት ሰጥተውታል፡፡ በተጨማሪ ታሪካዊ እና ለታላቁ ደብር ለደብረ ታቦር ኢየሱስ በወጣቶች የተሰራ ሰረገላ በዓሉን ካደመቁት ትእይንቶች መካከል አንዱ ነበር፡፡

ደብረ ታቦር ለሀገሪቱ ሊቃውንት መፍለቂያ በመሆን በምሳሌነት የሚጠሩ ካህናት እንደተለመደው ሁሉ የሚማርክ ጣዕመ ዝማሬአቸውና በአባቶችሽ ፈንታ ልጆችሽ ተተኩልሽ እንዳለ ነብዩ ከሊቃውንቱ እግር ሥር ቁጭ ብለው የተማሩ የሰንበት ት/ቤቶች ወጣቶች ዝማሬ አቅርበዋል፡፡ የደብረ ታቦር ከተማ ባህልና ቱሪዝም ጽ/ቤትም ለበዓሉ አከባበር የሚሆን የድምጽ ማጉያ በመስጠት እንዲሁም ከደብረ ታቦር ወረዳ ቤተ ክህነትና ማኅበረ ቅዱሳን ጋር በመተባበር የሀገሪቱን ባሕልና እሴት ተጠናክሮ እንዲቀጥል የበኩላቸውን አድርገዋል፡፡

የከተራ መርሐ ግብሩ ተጀምሮ እስከሚጠናቀቅ ድረስ የ4ቱ ጉባኤ መምህር የሆኑት የደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እንድርያስ ትምህርት፤ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጥተዋል፡፡ እርሳቸውም በዓለ ጥምቀት ቤተ ክርስቲያናችን ከምታከብራቸው አበይት በዓላት መካከል አንዱ መሆኑን ጠቅሰው ፤ ታቦቱ ወደ ጥምቀተ ባሕር ወርደው የሚያድሩበት ምክንያት እግዚአብሔር ወልድ በፈለገ ዮርዳኖስ መጠመቁ ምሳሌ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ በጥምቀቱም የሰው ልጅ ኃጢዓት የተደመሰሰበት፤ ከኃጢዓት ባርነት የወጣበት መሆኑን ገልጸው ምእመናን ዳግመኛ ወደ ኃጢዓት ባርነት እንዳይመለሱ መትጋ እንደሚገባቸው ገልጸዋል፡፡ የጥምቀትን በዓልን ስናከብር ድኅንነት ነፍስን የምናገኝበት ከኃጢዓት ጸድተን የዘላለም ሕይወት የምንወርስበት በመሆኑ በሰላምና በፍቅር እንድናከብረው አበክረው አሳስበዋል፡፡

በዓለ ጥምቀቱ የሚከበርበት አጅባር ሜዳ አራት የታቦታት መግቢያ በሮች ያሉት ሲሆን ለብዙ ዘመናት ቅድስት ቤተክርስቲያን እየተገለገለችበት ቆይታለች፡፡ ይሁን እንጂ በሀገረ ስብከቱና በወረዳ ቤተ ክህነቱ ፈቃድና እውቅና የተቋቋመ ኮሚቴ ቢኖርም የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ አለመኖሩ፤ በህዝቡ ዘንድ ስጋት የፈጠረ ጉዳይ ሆኗል፡፡ ስለሆነም የሀገር እና ቤተክርስቲያን ሀብት በመሆኑ የሚመለከታቸው አካላት ትኩረት ተሰጥቶት የይዞታ ማረጋገጫ ሊኖረው እንደሚገባ አባቶች እና የአካባቢው ምእመናን ገልጸዋል፡፡

 

06Epiphany19

የከተራ በዓል በጃንሜዳ በድምቀት ተከበረ

  ጥር 10/2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ 

የከተራ በዓል በጃን ሜዳ ቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዓን ሊቀነ ጳጳሳት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ የሰንበት ትምህርት ቤቶች መዘምራንና ምእመናን እንዲሁም የተለያዩ የውጭ ሀገራት አምባሳደሮችችና ሀገር ጎብኚዎች በተገኙበት በድምቀት ተከበረ፡፡06Epiphany19

06Epiphany20ከአሥራ አንድ ታቦታት በላይ ከየአብያተ

ክርስቲያናት በክብር በመውጣት በዝማሬና በእልልታ እንደታጀቡ ወደ ጃንሜዳ አምርተዋል፡፡ የእለቱ ተረኛ አዘጋጅ የሆነው የደብረ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን “ወረደ ወልድ እምሰማያት ውስተ ምጥማቃት፤ በፍስሐ ወበሰላም” በማለት እለቱን06Epiphany18 በማስመልከት ያሬዳዊ ወረብ አቅርበዋል፡፡ የደብሩ ፍቁረ እግዚእ ሰንበት ትምህርት ቤት አባላትም “በሰላም አስተርዐየ፡ አስተርዐየ ወልደ አምላክ፤ ወተወልደ በሀገረ ዳዊት ተወልደ፤ በዮርዳኖስ ተጠምቀ ከመይቤ ዘወነ” እያሉ ዝማሬ በማቅረብ በዓሉን አድምቀውታል፡፡

06Epiphany15

ስለበዓሉ አከባበር ከሰሜን አሜሪካ የመጣችው ሀገር ጎብኚ በዓሉን አስመልከተን ላቀረብንላት ጥያቄ ስትመልስ “ከዚህ በፊት ለአንድ ጊዜ የመስቀልን በዓል አከባበር ተመልክቼ ነበር፡፡ እሰከዛሬም ከምደነቅባቸው ሃይማኖታዊ በዓላት አንዱና ዋነኛው ነው፡፡ የጥምቀት በዓላችሁ ደግሞ የተለየ ነው፡፡ ልታከብሩትና ልትኮሩበት ይገባችኋል” ስትል አስተያየቷን ሰጥታለች፡፡

06Abune Mathias

 

በመጨረሻም ቅዱስነታቸው በሰጡት ቃለ ምእዳን “ጌታን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፈለገ ዮርዳኖስ በዮሐንስ እጅ ለመጠመቅ መጣ፡፡ ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመናት በላያችን ተጭኖ የነበረውን መርገመ ነፍስ መርገመ ሥጋን አስወግዶ በረከተ ነፍስ በረከተ ሥጋን ለማደል በዮርዳኖስ ተጠመቀ፡፡ ኃጢዓታችንንም አስወገደ፡፡ ከዲያብሎስ ቁራኝነትም አላቀቀን፡፡ ወደ ወገኖቹ መጣ ወገኖቹ ግን አልተቀበሉትም፡፡ ነገር ግን ለተቀበሉት የእግዚአብሔር ልጅ መባልን ሰጣቸው፡፡ የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን የመንግሥቱ ወራሾች እንድንሆን የተጠራነው በጥምቀት ነው” ብለዋል፡፡ 

 

06Epiphany1

የከተራ በዓል በድምቀት እየተከበረ ነው

ጥር 10/2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

የከተራ በዓል በመላው ኢትዮጵያ በድምቀት እየተከበረ ነው፡፡

ከየአብያተ ክርስቲያናቱ ታቦታት በብፁዓን ሊቀነ ጳጳሳት፤ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ በሰንበት ትምህርት ቤተ መዘምራንና ምእመናን ታጅበው ወደ ጥምምቀት ባሕር በማምራት ላይ ይገኛሉ፡፡
የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ፤ የቅዱስ በዓለ ወልድ፤ የታዕካ ነገሥት በዐታ ለማርያም፤ የመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም፤ የመንበረ መንግሥት ቅዱሰ ገብርኤል ታቦታት በአንድነት በመሆን ወደ ጃን ሜዳ በማምራት ላይ ይገኛሉ የሌሎቹም አድባራትና ገዳማት ታቦታት ወደ ጃን ሜዳ በመቃረብ ላይ ናቸው፡፡

06Epiphany1    06Epiphany2   06Epiphany3

 

 06Epiphany4