IMG 0062

ዝግጅት ለጥምቀት በዓል

 

IMG 0062የጥምቀት በዓል በኢትጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በታላቅ ድምቀት ይከበራል፡፡ የጥምቀት በዓልን በአደባባይ በማክበር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ብቸኛዋ ቤተክርስቲያን  ስትሆን ከተለያዩ ዓለማት የበዓሉ ታዳሚ ለመሆን የእምነቱ ተከታዮችና ቱሪስቶች ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት ወደ ጥምቀት በዓል ማክበሪያ ቦታዎች ይሄዳሉ፡፡ ከበዓሉ ቀደም ብሎ ለታቦታቱ ማረፊያና ለበዓሉ ማክበሪያ የተለያዩ ዝግጅቶች ይከናወናሉ፡፡
 ካህናትና ምእመናን  ለበዓሉ የሚስማማ ልብስ በመልበስ ታቦታቱን በማጀብ  ከከተራ ጀምሮ በዝማሬና በእልልታ እስከ ቃና ዘገሊላ ድረስ በታላቅ ድምቀት ያከብራሉ፡፡
ሰሞኑንም በሀገራችን የጥምቀት በዓል ማክበሪያ ቦታዎችና ታቦታቱ የሚጓዙበት መንገዶች ሲጸዱና ሲያሸበርቁ ሰንብተዋል፡፡ ጥቂት ቦታዎችን ለመጎብኘት ሞክረናል፡፡

አዲስ አበባ
በአዲስ አበባ ከተማ 46 የጥምቀት በዓል ማክበሪያ ቦታዎች አሉ፡፡ ወደነዚህ ቦታዎች የሚወስዱ መንገዶች ሁሉ እየጸዱ በኢትዮጵያ ባንዲራ፣ በዘንባባና በቄጤማ እያሸበረቁ ይገኛሉ፡፡
በአራዳና በጉለሌ ክፍለ ከተማ ቤተ ክህነቶች ያገኘነው መረጃ እንደሚገልጸው፡-
1.    በጃንሜዳ የጥምቀት በዓል ማክበሪያ ከአስራ አንድ ባላይ ታቦታት የሚያድሩ ሲሆን እነሱም መንበረ ፓትርያርክ ቅ/ቅ/ማርያም ገዳም፣ ታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም፣ መ/ፀ/ቅ/ሥላሴ፣ መ/መ/ቅ/ገብርኤል፣ ገነተ ጽጌ ቅ/ጊዮርጊስ፣ ቀጨኔ ደ/ሰ መድኃኔዓለም፣ መንበረ ልዑል ቅ/ማርቆስ፣ ወ/ነጎድጓድ ቅ/ዮሐንስ ፣ገነተ ኢየሱስ፣ መ/ህ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ አንቀጸ ምሕረት ቅ/ሚካኤል ሲሆን የ2006 ዓ.ም በዓል መንፈሳዊ አገልግሎት አቅራቢ ተረኛ የወ/ነጎድጓድ ቅ/ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡

IMG 0034IMG 0045

2.    ወረዳ 13 ቀበሌ 16 ቀበና ሼል አካባቢ ቀበና መድኃኔዓለምና ቀበና ኪዳነምሕረት
3.    በጉለሌ እንጦጦ ተራራ  መ/ፀ ር/አድባራት ቅ/ማርያም እና እንጦጦ ደ/ኃ/ቅ/ራጉኤል
4.    ሽሮ ሜዳ አካባቢ
መንበረ ስብሐት ቅ/ሥላሴ፣ ሐመረ ኖህ ቅ/ኪዳነ ምሕረት
5.    ወረዳ 11 ቀ. 27 ቁስቋም አካባቢ መ/ንግሥት ቁስቋም ማርያም
6.    አዲሱ ገበያ በላይ ዘለቀ መንገድ አካባቢ ደ/ሲና እግዚአብሔር አብ፣ መንበረ ክብር ቅ/ሚካኤል እና አቡነ ተክለሃይማኖት
7.    ጉለሌ አምባ ቅ/ኪዳነ ምሕረትና ድልበር መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን
8.   ወረዳ 11 ቀበሌ 20 ፡-ገርጂ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን፤ የረር ቅዱስ ኡራኤል ቤተ ክርስቲያን፤ ቦሌ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን
9.   ወረዳ 17 ቀበለሌ 24 /ለምለም ሜዳ/፡-ደብረ ምጽላል እግዚአብሔር አብ ቤተ ክርስቲያን፤
10.  ወረዳ 17 ቀበሌ 2 ወንድራይድ ት/ቤት አካባቢ፡- 7 አብያተ ክርሰቲያናት
11.  ወረዳ 28፡- ሰዓሊተ ምሕረት ቅድስት ማርያም፤ አቡነ አረጋዊ፤ ቅዱስ ኡራኤል
12.  ወረዳ 16/17 ቀበሌ 1፡- ደብረ እንቁ ልደታ ለማርያም፤
13.  ሎቄ ገበሬ ማኅበር፡- ሎቄ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ
14.  ወረዳ 17 ገበሬ ማኅበር፡- ቦሌ ቡልቡላ ቅዱስ ጊዮርጊስ
15.  ወረዳ 28 ገበሬ ማኅበር ቀበሌ 14/15 ሲኤም ሲ፡- ሰሚት ኪዳነ ምሕረት፤ ቀሬ ቅዱስ ጊዮርጊስ፤  ወጂ መድኀኔዓለም
16.  ቦሌ 14 /15፡- መካነ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል፤ የረር ቅዱስ ገብርኤል፤ የረር ጽርሐ አርያም ቅድስት ሥላሴ
17.  ወረዳ 28 ገበሬ ማኅበር፡-  ደብረ ኢያሪኮ እግዚአብሔር አብ
18.  ራስ ኃይሉ ሜዳ/ መድኀኔዓለም ትምህርት ቤት አካባቢ፡- ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል፤ ደብረ መዊዕ ቅዱስ ሚካኤል፤ ጽርሐ አርያም ሩፋኤል፤ ብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጼጥሮስ ወጳውሎስ፤ ጠሮ ሥላሴ
19.  ትንሹ አቃቂ ወንዝ/ ገዳመ ኢየሱስ/፡- ቀራንዮ መድኀኔዓለም፤ ደብረ ገሊላ ቅዱስ አማኑኤል፤ ቅዱስ ጳውሎስ፤ ገዳመ ኢየሱስ፤ ደብረ ምጥማቅ ቅዱስ ፊልጶስ፤ ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም፤ ፊሊዶር አቡነ ተክለ ሃማኖት
20.  አስኮ ጫማ ፋብሪካ / ሳንሱሲ አካባቢ፡- አስኮ ደብረ ገነት ቅዱስ ገብርኤል፤ ኩርፎ ቅዱስ ጊዮርጊስ
21.  ወረዳ 25 ቀበሌ 25 አካባቢ፡- ደብረ ከዋክብት አቡነ አረጋዊና ገብረ ክርስቶስ፤ ደብረ ይድራስ ቅዱስ ጊዮርጊስ፤ አውጉስታ ቅድስት ማርያም፤ ዳግማዊት ጸድቃኔ ማርያም፤
22.  ወረዳ 24 ቀበሌ 15፡- አየር ጤና ኪዳነ ምሕረት፤ ጀሞ ሥላሴ፤ ደብረ ራማ ቅዱስ ገብርኤል
23.  ቃሌ 15 ቀበሌ፡- ቃሉ ተራራ አቡነ ሃብተ ማርያም፤ ፍኖተ ሎዛ ቅድስት ማርያም
24.  አያት ቤተ ሥራዎች ድርጅት፡- መሪ አቡ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፡- መሪ ቅድስት ኪዳነ ምሕረት፤ ቅዱስ ሩፋኤል፤ መሪ ቅድስት ሥላሴ
25.  ወረዳ 28 ገበሮ ማኅበር፡- ኢያሪኮ እግዚአብሔር አብ
26.  ቤተል ኳስ ሜዳ፡- ደብረ ኢዮር ቅዱስ ሚካኤል፤ አንፎ ቅዱስ ኡራኤል
27.  ወረዳ 18 ቀበሌ 26፡- ቅዱስ እስጢፋኖስ፤ ደብረ ይባቤ ቅዱስ ያሬድ
28.  ወረዳ 16 ቀበሌ 11 ኳስ ሜዳ፡- ደብረ ጽጌ ቅዱስ ኡራኤል፤ የካ ቅዱስ ሚካኤል
29.  አድዋ ፓርክ፡-ቦሌ ደብረ ሰላም መድኀኔዓለም

IMG 0056

ከአዲስ አበባ ወጪ የሚገኙ አኅጉረ ስብከት በከፊል
  የበዓለ ጥምቀት ዝግጅት በጎንደር – ፋሲለደስ፡-
ቀሃ ኢየሱስ፤ ዮሐንስ መጥምቅ፤ አባ ጃሌ ተክለ ሃማኖት፤ እልፍኝ ቀዱስ ጊዮርጊስ፤ ፊት ሚካኤል፤ አጣጣሚ ሚካኤል፤ መንበረ መንግሥት መድኀኔዓለም
ፋሲለድስ መዋኛ ፡- 8 ታቦታት
ልደታ ለማርያም
በዓታ ለማርያም
   አቡነ ሐራ – ሩፋኤልን ዞሮ ይገባል
በጎንደር ዙሪያ በሚገኙ 13 ቀበሌዎች፤ 13 ክፍለ ከተማዎችና የገጠር ቀበሌዎች

በሐዋሳ  የበዓለ ጥምቀት ዝግጅት
ፒያሳ ሔቁ አካባቢ፡- ደብረ ምጥማቅ መድኃኔዓለም
ቅዱስ ገብርኤል
ቅድስት ሥላሴ
ፋኑኤል
በዓለ ወልድ
ዳቶ ኪዳነ ምሕረት
ሐዋሳ መግቢ በይርጋለም ሞኖፖል አካባቢ፡- ደብረ ምጥማቅ መድኃኔዓለም፤ አቡነ ተክለ ሃማኖት፤ ቅዱስ ጊዮርጊስ

የበዓለ ጥምቀት ዝግጅት በሚዛን ተፈሪ
በሚዛን ተፈሪ ከተማ በሚዛንና አማን ክፍለ ከተማ ለሚከበረው  በዓል ከከተራው  ጀምሮ የከተማዋን ዋና መንገድ በአረንጓዴ ቢጫ ቀይ ሰንደቅ ዓላማ  የማስዋብ ስራ በከተማው የእምነቱ ተከታይ ወጣቶች ተሰርቷል:: በከተማው የዘንድሮው የበዓሉን ዝግጅት ተረኛ የሆኑት የአቡነ ተክለሀይማኖት የእናቶች አንድነት ገዳምና የቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተ ክርስትያን ለታቦታት ማደርያና እንዲሁም ለስርኣተ ማኅሌቱና ቅዳሴው የሚከናወንበት ድንኳን በሰበካ ጉባኤያት አስተባባሪነት፣ በወጣት ሰንበት ተማሪዎች ፣ በሚዛን መዕከል አባላት፣ በሚዛን ግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችና በአካባቢው የሚገኙ የእምነቱ ተከታይ ወጣቶች ተባባሪነት የጥምቀተ ባህር ማክበርያ ቦታ ጽዳት ከተደረገ በኋላ ድንኳንና ሌሎች አስፈላጊ ቁሳቁሶችን በማቅረብ በዓሉን ለማድመቅ ተዘጋጅተዋል::
በዓሉ የሚከበረው በሁለት የጥምቀተ ባህር ስፍራዎች ኮሶኮልና አማን ጥምቀተ ባህር ናቸው፡፡  በሚዛን ክፍለ ከተማ ከሾርሹ በዓለ ወልድ አንድ ታቦት፣ ከሚዛን ደብረ ብስራት ቅዱስ ገብርኤል ሁለት ታቦታት፣ ከሚዛን ደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሁለት ታቦታት፣ ከሚዛን ማረሚያ ቤት ቅዱስ ሚካኤል  አንድ ታቦት በተለምዶ ኮሶኮል ወደሚባለው ጥምቀተ ባህር ጉዟቸውን የሚያደርጉ ሲሆን ፣ በአማን ክፍለ ከተማ ደግሞ ከደብረ መድኀኒት ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ሁለት ታቦታት፣ ከቅድስት ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን አንድ ታቦት፣ ከደብረ ሰላም ቅድስት ኪዳነ ምህረት ቤተ ክርስቲያን ሁለት ታቦታት፣ ከዛሚቃ አባ ሳሙኤል ገዳም አንድ ታቦት፣ ከቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን አንድ ታቦት ፣ ከመንበረ ንግስት ቅድስት ቁስቋም ቤተ ክርስቲያን አንድ ታቦት ወደ አማን ጥምቀተ ባህር እንደሚዎጡና በአጠቃላይ ቁጥራቸው አስራ አራት የሚሆኑ ታቦታት ወደ ሁለቱ ጥምቀተ ባህር እንደሚያመሩ መረጃዎች ይጠቁማሉ::
ወጣቶች እንደተለመደው ዘንድሮም ሕዝቡ በግፍያ እንዳይጎዳና መጨናነቅ እንዳይፈጠር ታቦታት በሚያልፉበት መንገድ ላይ ምንጣፍ እየተሸከሙ በማንጠፍ ባለፉት ጊዜያት ያሳዩት የነበረው አገልግሎት ዘንድሮም ለቤተ ክርስቲያናቸውና ለእምነታቸው ያላቸውን ፍቅርና ክብር ለማሳየት ተዘጋጅተዋል፡፡ /ከሚዛን ማዕከል ሚድያ ክፍል/

የጥምቀት በዓል ዝግጅት በወልድያ
በወልድያ ከተማ የጥምቀት በዓል ከዋዜማው ጥር 10 ቀን 2006 ዓ.ም ጀምሮ በድምቀት እንደሚከበር ተገለፀ፡፡
የሰሜን ወሎ ሃገረ ስብከት የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ ክፍል ኃላፊና የወልድያ ወረዳ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ መልአከ ኃይል ስጦታው ሞላ የበዓሉን አከባበር አስመልክተው በሰጡት መረጃ በከተማው ውስጥ ያሉ አድባራትና በዙሪያው የገጠር አብያተ ክርስቲያናት የከተራ በዓሉን በወልድያ ታቦት ማደሪያ በአንድ ላይ ያከብራሉ፡፡
በከተማውና በዙሪያው ያሉ የ10 አብያተ ክርስቲያናት 15 ታቦታት ከቀኑ 7፡00 ጀምሮ ወደ ታቦት ማደሪያው እንደሚንቀሳቀሱና ምዕመናንም በሰዓቱ ተገኝተው የሚከብሩ ሲሆን፤ ምዕመናን በዓሉን በሰላምና በፍቅር እንዲሁም ጧሪ የሌላችውን አረጋዊያንና አሳዳጊ የሌላቸው ህፃናትን በመርዳት እንድያከብሩ ሥራ አስኪያጁ ገልፀዋል፡፡
ከባለፉት ሁለትና ሦስት ዓመታት ወዲህ በበዓላት አከባበር ወጣቱ እያሳየው ያለው ተሳትፎና ሥነ-ስርዓት እጅግ የሚያስደስት በመሆኑ በዚህ ዓመትም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የሚጠበቅ ሲሆን፤
ታቦታቱ ጉዞ የሚያደርጉበትን ጎዳናዎች በማፅዳት፣ ሠንደቅ ዓላማዎችን በመስቀል፣ ምንጣፍ በማንጠፍና ቄጤማ በመጎዝጎዝ ለእግዚአብሔር ያላቸውን ፍቅር እየገለፁ ይገኛሉ፡፡ በዓሉን ለማክበር ሰ/ት/ቤቶች፣ ማኅበራትና ወጣቶች ዝግጅት በማድረግ ላይ ናቸው፡፡
በአጠቃላይ በዕለቱ መዝሙር፣ ዕለቱን የተመለከተ ስብከተ ወንጌልና ልዩ ልዩ መርሐ ግብሮች ከተካሄዱ በኋላ 11፡30 ላይ ታቦታቱ ወደ ተዘጋጀላቸው ማረፊያ ይገባሉ፡፡ በዚሁ የዋዜማ በዓሉ ፍፃሜ ይሆናል፡፡ /ወልድያ ማዕከል  ሚድያ ክፍል/

 

 

ቅዱስ ፓትርያርኩ ምእመናን ለመዋቅራዊ ለውጡ ድጋፍ እንዲሰጡ ጠየቁ

 

 

ጥር 9/2006 ዓ.ም.

 

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ጥር 7 ቀን 2006 ዓ.ም. የቅድስት ሥላሴን ዓመታዊ የንግሥ በዓል በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በከበረበት ወቅት ቤተ ክርስቲያኗ በለውጥ ላይ በመሆኗ ምእመናንና አገልጋይ ካህናት ለውጡን ተግባራዊ ለማድረግ እንዲተባበሩ ጥሪ አስተላለፉ፡፡

ቅዱስነታቸው የዕለቱን በዓል አስመልከተው ጥልቅ መንፈሳዊ ትምህርት ካስተማሩ በኋላ በትምህርታቸው ማጠቃለያም ቤተ ክርስቲያን የምእመናንንና የካህናት በመሆኗ የሁለቱ አንድነት አገልግሎቱን የተሟላና የሠመረ እንደሚያደርገው ገልጸው በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተንሰራፍቶ ያለው ተገቢ ያልሆነ አሠራር መስተካከል እንደሚኖርበት አሳስበዋል፡፡

 

ቅዱስነታቸው በተደጋጋሚ ተገቢ ያልሆነ አሠራር መኖሩ እየተነገረ ዝም ብሎ ማለፍ ስለማይገባ የችግሩን አሳሳቢነት ግምት ውስጥ በማስገባት የቤተ ክርስቲያኗን አሠራርና መዋቅር በተመለከተ ለውጥ ላይ ስለምትገኝ ምእመናንም የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ጠይቀዋል፡፡አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ጠይቀዋል፡፡

 

 

 

 

 

የአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት መዋቅራዊ ለውጡን እንደሚደግፉ አስታወቁ

ጥር 9/2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

• “የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ቤተ ክርስቲያኗ የምታምንባችሁ፤ እናንተም የቤተ ክርስቲያኒቱ ታማኝ ልጆች እንደሆናችሁ እናምናለን፡፡” /ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ /
• በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ተንሰራፍቶ ያለውን ሙስና፤ ዘረኝነት፤ ብልሹ አሠራሮች አንገታችንን ደፍተን እንድንሔድ አድርጎን ነበር፡፡/የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች/

የአዲስ አባባ ሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ሓላፊዎችና አባላት በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የተንሠራፋውን ብልሹ አስተዳደር፤ ሙስናና ዘረኝነትን ያስተካክላል ተብሎ የተዘጋጀውን አዲሱን መዋቅራዊ ለውጥ እንደሚደግፉ ጥር 8 ቀን 2006 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሸ ቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት አስታወቁ፡፡

ተወካዮቹ በመግለጫቸው “በርካታ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት እስከ እስር ድረስ በመድረስ ሲታገሉለት የነበረውንና አይነኬ የሚመስለውን በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ የተንሰራፋውን ብልሹ አሠራርን እናወግዛለን፡፡ እነዚህን ዘርፈ ብዙ ችግሮችን ለመቅረፍ በሚደረገው ጥረት ውስጥም በግንባር ቀደምትነት እንሰለፋለን፡፡ እስካሁን በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ተንሰራፍቶ ያለውን ሙስና፤ ዘረኝነት፤ ብልሹ አሠራሮች አንገታችንን ደፍተን እንድንሔድ አድርጎን ነበር፡፡ ዛሬ የቤተ ክርስቲያናችን ትንሣኤ ደርሷል፡፡ የጥንቷን ቤተ ክርስቲያናችን ክብር እንደሚመለስልን እናምናለን፡፡ እኛም ከቅዱስነትዎና ከቅዱስ ሲኖዶስ ጎን በመሰለፍ የሚጠበቅብንን ለማበርከት ተዘጋጅተናል” ብለዋል፡፡

የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በሚደረጉ ብልሹና ሥነ ምግባር የጎደላቸው ድርጊቶች ሲፈጸሙ በመጋፈጥ ፊት ለፊት በመናገራቸው አንዳንድ የደብር አለቆችና ጸሐፊዎች በቀጥታ ለፖሊስ በመጻፍ አባላት እየተደበደቡና እየታሰሩ እንደሚገኙ የገለጹት አባላቱ አንዳንድ ፖሊሶችም ጉዳዩን ሳያጣሩ የድርጊቱ ተባባሪ እንደሚሆኑ ተናግረዋል፡፡ ለዚህም ማሳያነት በአሁኑ ወቅት በደብረ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ያለውን ችግር በተወካዩ አማካይነት አቅርበዋል፡፡

ከዚህ በፊት በሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት አማካይነት ለቅዱስ ሰሲኖዶስ ቀርቦ የነበረውና በእንጥልጥል የቀረው የተሐድሶ መናፍቃንን ጉዳይ በተመለከተ ተጨባጭ መረጃዎችን ማቅረባቸውንና የተወሰኑ ግለሰቦችና ማኅበራት ተወግዘው መለየታቸውን አስታውሰዋል፡፡ ነገር ግን ውሳኔ ሳይሰጣቸው የቀሩ ግለሰቦችና ማኅበራት ስለሚገኙ በቀረበው ማስረጃ መሠረት ጉዳዩ ታይቶ ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ እንዲሰጥበትም ጠይቀዋል፡፡

 

መናፍቃኑ በየብሎጎቻቸው ቅዱሳንን እየተሳደቡ እንደሚገኙና በአሁኑ ወቅት የገጠር አብያተ ክርስቲያናትና አብነት ትምህርት ቤቶች ላይ በመዝመት የራሳቸውን መምህራንን በማሰልጠንና በመቅጠር ወረራ እያካሔዱ እንደሚገኙ በመጥቀስ መፍትሔ እንዲፈለግለት አሳስበዋል፡፡

ቅዱስነታቸው በሰንበት ትምህርት ቤት ተወካዮች ለቀረቡላቸው ጥያቄዎችና አስተያየቶች ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ “የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ቤተ ክርስቲያኗ የምታምንባችሁ፤ እናንተም የቤተ ክርስቲያኒቱ ታማኝ ልጆች እንደሆናችሁ እናምናለን፡፡ ምክንያቱም ሰንበት ትምህርት ቤት ዓለማቀፋዊ ነው፡፡ ሁሉም ወጣት በሰንበት ትምህርት ቤት እንዲታቀፍ ነው የምንመኘው፡፡ መበርታት አለባችሁ፡፡ በቤተ ክርስቲያን ላይ የተደነቀረውን መሠናክል የገንዘብ ብክነት፤ የአስተዳደር ብልሹነትን ለመቅረፍና አማሳኞችን ለመታገል እናንተ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት መዝመት አለባችሁ፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ሀብት ባክኗል፤ መልካም አስተዳደር የለም፤ ሸፍጥና ጉቦ ተንሰራፍቷል፡፡ ሃቀኝነት አይታይም፡፡ ይህንን ለመከላከል ትጉ” ብለዋል፡፡
ከቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ውጪ የሚያስተምሩና ችግር የሚፈጥሩ ካሉ በተረጋገጠ መረጃ አስደግፈው ማቅረብ እንደሚገባቸው የገለጹት ቅዱስነታቸው፤ የማኅበራት ደንብን አስመልኮቶ ወጣቱ በአንድ ሕግ፤ በአንድ ሰንበት ትምህርት ቤት መታቀፍ እንዳለበት ጠቅሰው፤ ቤተ ክርስቲያንም ይህንን ጉዳይ ዝም ብላ እንደማትመለከተው አሳስበዋል፡፡

ቅዱስነታቸው ከሰንበት ትምህርት ቤቶች ጋር በየአጥቢያው የሚፈጠሩ ችግሮች ምን እንደሆኑ መታወቅ እንዳለባቸው በመግለጽ “ለምንድነው የምትታሰሩት? ማነው የሚያሳስራችሁ? ተጽእኖስ ለምን ይደርስባችኋል? ይህ ጉዳይ መጣራት አለበት፡፡ ችግሩ የማነው? ከነማስረጃው አቅርቡ፤ ቤተ ክርስቲያን መፍትሔ ትሰጣለች፡፡ ልጆቿን ዝም ብላ አሳልፋ አትሰጥም” ብለዋል፡፡

 

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የአደረጃጀት መዋቅር እንዲጸድቅ በዕንባ ተጠየቀ

 ጥር 6/2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

  • ቅዱሰ አባታችን ለልጆቼ ምን ላውርሳቸው? ሙስናን? የምእመናን ተወካይ
  • የቤተ ክርስቲያኗን አስተዳደር እናስተካክላለን ብለን ከዚህ ደርሰን ወደኋላ እንመለሳለን ማለት ዘበት ነው፡፡ በጭራሽ አይሞከርም!!! ሐቋንም ይዤ እጓዛለሁ!!!  ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ያስጠናው መዋቅራዊ ለውጥ ቤተ ክርስቲያናችንን ወደ ተሻለ ልማት ያራምዳል፤ ሙስናን ያጠፋል፤ወደ ሌላ በረት የገቡትን በጎች ይመልሳል፤ እኛም የቤተ ክርስቲያን አካል በመሆናችን የተሻለ አገልግሎት እንድንሰጥ የሚያደርገን በመሆኑ በአስቸኳይ ተግባር ላይ እንዲውልልን በማለት በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሚገኙ ምእመናን ጥር 5 ቀን 2006 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ለቅዱስ ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በንግግርና በእንባ ጠየቁ፡፡

ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ጀምሮ ምእመናን በጠቅላይ ቤተ ክህነት ግቢ ውስጥ መሰባበሰባቸውን ቀጥለዋል፡፡ የምእመናኑ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት በቅዱስ ፓትርያርኩ ልዩ ጽ/ቤት በመገኘት ምእመናን የሚያቀርቡት ጥያቄ እንዳላቸውና ይህንንም ለማቅረብ እንዲችሉ ፈቀዳቸውን ለመጠየቅ ቀርበዋል፡፡ የቅዱስነታቸው ልዩ ጽ/ቤት በርካታ ምእመናንን ማስተናገድ ስለማይችል 60 ምእመናን ብቻ እንዲገቡ ተፈቀደ፡፡ ሆኖም ግን በግቢው ውስጥ ቁጥራቸው ከ500 በላይ ምእመናንና ምእመናት በመገኘታቸው የጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ እንዲፈቀድ ተደርጎ ምእመናንን ወደ አዳራሹ በመግባት ቦታቸውን ያዙ፡፡

ቅዱስነታቸው ምእመናኑን ለማነጋገር ፈጠን ፈጠን እያሉ ወደ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ገብተው በመምጣት በግራም፤ በቀኝም የሚገኙትን ምእመናንን እየባረኩ ቦታቸውን ከያዙ በኋላ መርሐ ግብሩን በጸሎት ከፍተዋል፡፡
ከጸሎት በኋላ የምእመናን ተወካዮች ለቅዱስነታቸው ጥያቄዎቻቸውን በጽሑፍ ማቅረባቸውን ቀጠሉ፡፡

“በአኩሪ ታሪክና ምግባር የምትታወቀው ቤተክርስቲያናችን የዘመናት ስሟንና ክብሯን የማይመጥን እኩይ ተግባራት የሚፈጸምባት ቦታ፤ ከሃይማኖት ይልቅ ግላዊ ጥቅም በሚያስቀድሙ የውስጥ አርበኞች ብልሹ አሠራር፤ ዘረኝነት፤ ሙስና እና የሥነምግባር ጉድለት ጎልቶ የሚታይባትና ተከታዮቿን የሚያሸማቅቅ ተግባር የሚፈጽሙባት እየሆነች መጥታለች” በማለት በእድሜ ገፋ ያሉ አዛውንት በንባብ ገለጹ፡፡

የውስጥ የቤተክርስቲያን ጠላቶች ያሏቸውንም መለያቸውን ሲገልጹ፡- “ዘመናዊ የፋይናንስ ሥርዓት ኃላፊነትና ተጠያቂነት ሥራ ላይ እንዳይውል በጥብቅ ይከላከላሉ፤ ከአጥቢያ ጀምሮ እስከ ሀገረ ስብከት እንዲሁም ጠቅላይ ቤተ ክህነት ድረስ በተዘረጋ የሙስና መረብ ከሕጋዊ መዋቅሩ በበለጠ እርስ በእርስ በመደጋገፍ፤ የተፈጸሙ ጥፋቶችን ይሸፋፈናሉ፤የሥራ ዕድገት በሙያና በትምህርት ብቃት ላይ የተመሠረተ ሳይሆን በዘመድና በጉቦ እንዲፈጸም ያደርጋሉ፣ ጥፋተኛነቱ የተረጋገጠ የደብር አለቃ ወይም ኃላፊ ላይ ተገቢውን የሥነ ሥርዓት ዕርምጃ በመውሰድ ፋንታ ወደ ሌላ የተሻለ ቦታ እንዲዘዋወሩ ይደረጋል” በማለት በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እየተካሔደ ያለውን ብልሹ አሠራር ተቃውመዋል፡፡

አዛውንቱ ቀጥለውም በአሁኑ ወቅት በሰፊው የሚስተዋለው የሥነ ምግባር ግድፈቶች፣ ጎጣዊ/ዘረኛ አሠራሮችና የሙስና መንሰራፋት ለመምዕመናን ወደ መናፍቃን ጎራ መጉረፍ ምክንያት ከመሆናቸውም ባሻገር ፤በቁጥራቸው ጥቂት የማይባሉ የቤተክርስቲያን አገልጋዮች የተጠናና የተደራጀ በሚመስል ሁኔታ የሚፈጽሙትን የሥነ ምግባር ጉድለቶች በማየት አንዳንድ ምዕመናን ከቤተክርስቲያን እየራቁ እንደሚገኙ ጠቁመዋል፡፡

“የአደረጃጀትና የአሠራር ማሻሻያ ጥናቱ ተግባራዊ ሆኖ ቤተክርስቲያኒቱን ሰንገው አላንቀሳቅስ ያሏት ሙስናና ጎጠኝነት ተወግደው፤ ምዕመናን ለቤተክርስቲያን የሚሰጡት ገንዘብ ለታለመለት ዓላማ ለማዋል ያስችላል ተብሎ በጉጉት ሲጠበቅ፤ በጥናቱ ያልተደሰቱ የተወሰኑ ግለሰቦች ባቀረቡት ቅሬታ ጥናቱ ተግባራዊ ከመሆን ታግዶ እንደገና ባዲስ መልክ እንዲታይ መወሰኑን በከፍተኛ ድንጋጤ ነው የሰማነው፡፡ በቤተክርስቲያኒቱ ውስጥ ተንሠራፍቶ የቆየው ሙስናና ብልሹ አሠራር ጊዜ ሊሠጠው የማይገባ ለነገ ሊባል የማይችል ባስቸኳይ ርምጃ መወሰድ ያለበት ስለሆነ የቤተክርስቲያቱን ሥር የሰደደና የተከማቸ ችግር ያስወግዳል ተብሎ ተስፋ የተጣለበትና የቤተክርስቲያኒቱ የበላይ አካል በሆነው በቅዱስ ሲኖዶስ የጸደቀው ጥናት ባስቸኳይ ተግባራዊ እንዲደረግ በአጽንኦት እንጠይቃለን” ብለዋል፡፡

የተቋማዊ ለውጡ ጥናት በቅዱስ ሲኖዶስ ተቀባይነት ማግኘቱ በራሱ ከፍተኛ ውጤት ቢሆንም አስፈላጊው የአፈጻጸም ስልትና በቁርጠኝነት ሥራ ላይ ሊያውል የሚችል ቅን ታታሪ ታማኝ ተግዳሮቶችን በከፍተኛ ጽናት መቋቋም የሚችል የሰው ኃይል ካልተመደበለት ብልጣብልጦቹ እጅ ወድቆ የታሰበውን ውጤት ሳያስገኝ ሊከሽፍ እንደሚችል የጠቆመው መግለጫው፤ ተቋማዊ ለውጡን በተሟላና በተሳካ ሁኔታ ሥራ ላይ ለማዋልና ዘለቄታማነቱን ለማረጋገጥ ይቻል ዘንድ ትኩረት ያስፈልጋቸዋል ያሏቸውን ነጥቦች በዝርዝር አቅርበዋል፡፡

  1. በጥናቱ ላይ ጥያቄ ያለው ግለሰብ ወይም ቡድን ቢኖር ጥያቄውን በዝርዝር አቅርቦ በጥናት ቡድኑ ታይቶ በቅዱስ ሲኖዶስ የሚታመንበት ነገር ካለ አስፈላጊው ማሻሻያ ከሚደረግበት በስተቀር በጉጉት የምንጠብቀው የጥናት ውጤት ቢቻል ለማስቆም ካልተቻለም ለማዘግየት እንደገና በአዲስ መልክ እንዲታይ እየተደረገ ያለው አካሄድ ቆሞ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ልዕልና ተጠብቆ በውሳኔው መሠረት እንዲፈጸም እንዲደረግ፤
  2. የተጠናውን የአሠራርና የአደረጃጀት ጥናት የሚገመግም አዲስ ኮሚቴ በተመለከተም ጥናቱን ሊያዳብር በሚችል መልኩ በፍጥነት ሰርተው ያቀርባሉ ብሎ ለማሰብ ከኮሚቴው አባላት መካከል ከአሁን ቀደም በሀገረ ስብከቱም ሆነ በጠቅላይ ቤተክህነት ውስጥ በተመሳሳይ ችግር ተጠቃሽ የሚሆኑ ሰዎች መካተታቸው ያሳሰበን በመሆኑ እንደገና እንዲታይልን እንዲደረግ
  3. ተቋማዊ ለውጡን አስመልክቶ ቅዱስ ሲኖዶስ ያስተላለፈው ውሳኔ እንዳይፈጸም በሚያውኩና በሚቃወሙ ላይ ሌሎችን ሊያስተምር የሚችል ጥብቅ የሥነ ሥርዓት ርምጃ እንዲወሰድ እንዲደረግ፤
  4. ከቅን የቤተክርስቲያን አገልጋይ ካህናትና ሠራተኞች፣ ከሰንበት ት/ቤት እንዲሁም ከምዕመናን የተውጣጣ ተጠሪነቱ ለቅዱስ ሲኖዶስ የሆነ የተቋማዊ ለውጥ አስፈጸሚ አካል እንዲቋቋም፤
  5. ከዚህ ቀደም በቤተክርስቲያን ሀብትና ንብረት ላይ ከፍተኛ ምዝበራ የፈጸሙ ሁሉ ጉዳያቸው ተጣርቶ ተገቢው ሕጋዊ እርምጃ እንዲወሰድልን፣
  6. ስለ ጎጠኝነትና ሙስና አስከፊነት የሥልጠናና ትምህርት መርሃ ግብር ቀርጾ ተግባራዊ እንዲደረግ፣
  7. ከሙስና የጸዱትንና የላቀ መልካም ተግባር የሚፈጸሙትን አገልጋዮች በመሸለም እንዲበረታቱ እንዲደረግ፣
  8. ቤተክርስቲያኒቱ ከወቅታዊ ሁኔታዎች አንጻር እራሷን እየፈተሸች፣ ችግሮቿን እየለየች መፍትሔ በማስቀመጥ ተግባራዊ እርምጃ ለመውሰድ የሚያስችላት የጥናትና ምርምር ማዕከል እንዲቋቋም እንዲደረግ፣
  9. ከመንግሥት አሠራር ልምድ በመቅሰም በስፋት የተንሰራፋውን የሙስና ተግባር መቋቋም ይቻል ዘንድ የሥነ ምግባርና ጸረ ሙስና አካል ከጠቅላይ ቤተክህነት እስከ አጥቢያ ቤተክርስቲያን እንዲቋቋም እንዲደረግ በቅድስት ቤተክርስቲያናቸን ስም አበከረን እንጠይቃለን በማለት በመግለጫቸው አቅርበዋል፡፡

በተጨማሪም በቅዱስነታቸው ፈቃድ የምእመናን ተወካዮች ጥናቱን አስመልከቶ ሀሳባቸውን ከገለጹት መካከል፡-

“ይህ አዲስ መዋቅር ቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ብዝበዛን፤ የአስተዳደር ብልሹነትን፤ ግማሹ እያለቀሰ ሌላው እየተደሰተ እንደፈለገ እየሆነ ያለበት አስቸጋሪ ሁኔታን የሚያስተካክል ነው፡፡ የዚህ መዋቅር መውጣት የሚያስደነግጣቸው ይኖራሉ፡፡ ምክንያቱም የገንዘብ ብዝበዛን፤ ብልሹ አስተዳደርን ስለሚያስቆም በዚህ ሕይወት ውስጥ የበለጸጉና ከፍተኛ ጥቅማጥቅሞችን ያገኙ የነበሩ ግለሰቦች የለመዱት ሲቋረጥባቸው ሊደነግጡ ይችላሉ፡፡ እንኳን ቤተ ክህነት በቤተ መንግሥት ውስጥ አዳዲስ አሠራሮች ለሀገርና ለሕዝብ የሚጠቅሙ ጉዳዮች ሲነሱ ሁሉም እልል ብሎ አይቀበልም፡፡ ይህ የመዋቅር ጥናት በቤተ ክርስቲያናችን ታሪክ ውስጥ ታላቅ ምእራፍ የከፈተ ነውና እርስዎ ጀምረውታል፤ ለስምዎ፤ ለታሪክዎና ለቤተ ክርስቲያኗ ሕልውና ሲሉ ያስፈጽሙት፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ከብዝበዛ ያድኗት፤ ከፍጻሜም ያድርሱት” በማለት የእድሜ ባለጸጋና ቀድሞ ቃለ ዓዋዲን ካረቀቁ ሊቃውንት መካካል የነበሩ አባት እንባ እየተናነቃቸው ተናግረዋል፡፡

አንድ እናትም ንግግራቸውን ቀጠሉ “የእግዚአብሔር ዓላማ የጠፉትን ወደ ቤቱ ለመመለስ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን ትንሣኤ ደርሷል ብለን እናምናለን፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን ችግር በሚገባ አውቀናል፤አዝነናል፤ አልቅሰናል፤ ዋጋችንንም አግኝተናል፤ ተቀጥተናል ይበቃናል፡፡ ልጆቻችን ቤተ ክርስቲያናችንንና እምነታችንን ይረከቡ ዘንድ እኛ ወላጆች ድልድዮች ነን፡፡ቤተ ክርስቲያናችንን ለልጆቻችን ለማስረከብ እንድንችል ይርዱን፡፡ቅዱስ አባታችን ለልጆቼ ምን ላውርሳቸው? ሙስናን??? ቅዱስ አባታችን ቤተ ክርስቲያን አሁን በሌላ በረት ያሉ ልጆቿን የምትሰበስብበት ሰዓት ደርሷል፡፡ይህ ጥናት ተግባራዊ ቢሆን የጠፉ ልጆቿ በሕይወት ይኖራሉ፡፡በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተሰበሰብነው ምእመናንን እንዳንበተን ይህ መዋቅር በቶሎ ተግባራዊ ይደረግልን” በማለት እያለቀሱ ተማጽነዋል፡፡

ቅዱስነታቸውም ለቀረቡት የምእመናንን ጥያቄዎች በማረጋጋት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ “ይህንን ጉዳይ ገና ከመግባቴ ያወጅኩት እኔ ነኝ፡፡ሙስና፤ የገንዘብ ብክነት፤ ሓላፊነት የጎደለው አስተዳደር እንዲጠፋና መልካም አስተዳደር፤ ሓላፊነትና ተጠያቂነት ያለው አሠራር እንዲሰፍን መሥራት አለብን፡፡ አንድ ጥናት የተወሰኑ ሰዎች ያጠኑታል፡፡ ከዚያም ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንዲያዩት ይደረጋል፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የቤተ ክርስቲያንን ቋንቋ፤ ባሕል ተመርኩዘው ቢያጠኑት ይጠነክራል፡፡ ለቅዱስ ሲኖዶስ ቀርቦ ይጸድቃል፡፡ በፍጹም ስጋት አይግባችሁ፤ ጩኸቱ የእኔ ነው፡፡ ተጠናክሮ እንጂ ተዳክሞ አይመጣም፡፡

ቤተ ክርስቲያን ትክክለኛ መስመሯን እንድትይዝ ነው ፍላጎታችን፡፡ የቤተ ክርስቲያኗን አስተዳደር እናጠራለን፤ እናስተካክላለን ብለን ከዚህ ደርሰን ወደኋላ እንመለሳለን ማለት ዘበት ነው፡፡ በጭራሽ አይሞከርም!!! ሐቋን ይዤ እጓዛለሁ!!! እናንተም ደግፋችሁን ቤተ ክርስቲያናችን የቀድሞ ቅድስናዋን መመለስ አለብን፡፡ ስለዚህ የቤተ ክርስቲኗ ሊቃውንትና የዘመናዊውን የአስተዳደር ትምህርት የተማሩ ምሁራን ተቀናጅተው፤ አይተውት ጠርቶ እንዲመጣ ይደረጋል፡፡ ችግር ካለበት ያኔ ሀሳብ ልንሰጥበት እንችላለን፡፡አይዟችሁ አትፍሩ” በማለት ምእመናንን በማረጋጋት ባርከው የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል፡፡ ምእመናንም እግዚአብሔር ይመስገን ይህችን ቀን ቀድሶ ለሰጠን እያሉ በመዘመር ቅዱስነታቸውን ሸኝተዋል፡፡

አትሮንስ የመጻሕፍት ንባብ ውይይት ተካሔደ

ጥር 6/2006 ዓ.ም.

በማኅበረ ቅዱሳን የኤዲቶያል ቦርድ መጻሕፍት አርትኦት ክፍል አማካኝነት በየወሩ የሚቀርበው አትሮንስ የመጻሕፍት ንባብ ውይይት ጥር 4 ቀን 2006 ዓ.ም. በማኅበሩ የመሰብሰቢያ አዳራሽ ተካሔደ፡፡

በዕለቱ ለውይይት የቀረበው መጽሐፍ በመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ ተርጓሚነት የተዘጋጀው የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የሰባቱ ጊዜያት የሃይማኖትና የጸሎት መጽሐፍ ሲሆን መጽሐፉን ገምግመው ለውይይት ያቀረቡት ዲ/ን አሻግሬ አምጤ ናቸው፡፡ ውይይቱ ከመጽሐፉ ኅትመት ጥራት፣ ይዘት፣ አቀራረብና ከዋቢ መጻሕፍት አጠቃቀም አንጻር ጠንካራና ደካማ ጎኖችን በማንሳት ሰፊ ውይይት ተደርጎበታል፡፡ የጉባኤው ተሳታፊዎችም ከውይይቱ ትምህርትና ልምድ ለመቅሰም እንዳስቻላቸው ጠቁመው፤ ይህ በየወሩ የሚካሔደው የመጻሕፍት ውይይት ቀጣይነት እንዲኖረውና ሌሎችም መጻሕፍት አዘጋጆች ቢጋበዙ መልካም እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

በቀጣይነት የአትሮንስ የመጻሕፈት ንባብ መርሐ ግብር ውይይት የሚደረግበት መጽሐፍ “የኢትዮጵያ እምነት በሦስቱ ሕግጋት” የሚለው የአለቃ አያሌው ታምሩ እንደሆነ ከክፍሉ አስተባባሪ ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

“ማኅበረ ቅዱሳን የመዋቅር ለውጡ ለቤተ ክርስቲያን እንደሚያስፈልጋት ያምናል፡፡”

 አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ

 

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በቤተ ክርስቲያን ያሉትን ብልሹ አሠራሮች ለማስተካከል፤ የሰው ኃይል ምጣኔ፤ የንብረት አጠቃቀምና አያያዝ፤ በሌሎችም ዘርፎች እየታዩ ያሉትን ችግሮች ይፈታል ተብሎ የታሰበ ጥናት በማስጠናት ከቅዱስ ሲኖዶስ እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ድረስ በማቅረብ እንዲተችና ገንቢ አስተያየቶች እየተሰጡት ይገኛሉ፡፡ ሆኖም በአንዳንድ የቤተ ክርስቲያኒቱ አገልጋዮች ተቃውሞ ሲገጥመው ተስተውሏል፡፡ ይህም ጥናቱን ያጠናው ማኅበረ ቅዱሳን ነው በማለት በአገልጋዮችና ምእመናን ላይ ብዥታን ሲፈጥር ተመልክተናል፡፡ ይህንን ጥናት ማኅበረ ቅዱሳን አጥንቶታል? ቢያጠናስ ችግሩ ምንድነው? ለሚሉና ተያያዥ ጥያቄዎች ምላሽ እንዲሰጡን የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ የሆኑትን አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝን አነጋግረናል፡፡

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ያስጠናውን የመዋቅር ጥናት ማኅበረ ቅዱሳን እንዴት ይመለከተዋል?
አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ፡- ማኅበረ ቅዱሳን ጥናቱን በዝርዝር አያውቀውም፡፡ ነገር ግን ዘመኑን የዋጀ አሠራር ሀገረ ስብከቱ እንደሚያስፈልገው እናምናለን፡፡ የሀገረ ስብከቱን አገልግሎት ጠንካራ እና የበለጠ ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችሉ አሠራሮች ሁልጊዜም እየተተገበሩ መሄድ አለባቸው፡፡ ከዚህ አንጻር ማኅበረ ቅዱሳን የዚህ ጥናት ዝርዝር መረጃ ባይኖረውም ይደግፈዋል፡፡ ለቤተ ክርስቲያናችንም ያስፈልጋታል ብሎ ያምናል፡፡

አንዳንዶች የመዋቅር ጥናቱን ያጠናው ማኅበረ ቅዱሳን ነው ይላሉ፡፡ ይህ ምን ያህል እውነት ነው?
አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ፡- ይህን ጥናት በተመለከተ ማኅበሩ እንዲያዘጋጅ ከሀገረ ስብከቱ የተጻፈለት ደብዳቤ አልደረሰውም፡፡ አልተጠየቀም፡፡ ከዚህ በፊት አንዳንድ ጥናቶች ሲያስፈልጉ ማኅበሩ በደብዳቤ ይጋበዛል፡፡ አዘጋጅቶ ያስረክባልም፡፡ይህንን የመዋቅር ለውጥ ግን እንዲያጠና አልተጋበዘም፡፡

ማኅበሩ ተጋብዞ ባያጠናም ከአጥኚዎቹ መካከል የማኅበሩ አባላት የሉም?
አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ፡- ማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ዓላማ የተማረውን ወጣት ትውልድ ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲቀርብ ማድረግ፤ ለቤተ ክርስቲያን ጥሩ አመለካከት እንዲኖረው ማድረግ፤ ለማገልገል ክህሎት እንዲኖረው ማስቻል ስለሆነ በመንግሥትም ሆነ በግል ዩኒቨርሲቲዎች በሚገኙ ግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችንእያስተማረ ያስመርቃል፡፡ ከዚህ አንጻር በግቢ ጉባኤያት ተምረው፤ በማኅበሩ አባልነት ተመዝግበው በተለያዩ የቤተ ክርሰቲያን መዋቅር የሚያገለግሉ ባለሙያዎች ከያሉበት አጥቢያ ተጠርተው ይህንን የመዋቅርና የአሠራር ለውጥ ካዘጋጁትና ከሠሩት መካከል አብዛኛዎቹ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ናቸው፡፡ እነዚህ አባላት ጥናቱን ለመሥራት ሲጋበዙ ከማኅበረ ቅዱሳን ደብዳቤ ተጽፎላቸው ወይም ማኅበሩ ወክሏቸው አይደለም፡፡

ማኅበሩ እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነቱ ተጋብዞ የማጥናት መብት የለውም?
አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ፡- ማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያን አካል በመሆኑ መብት አለው፡፡ ይህ ሁሉ ባለሙያ ወደ ማኅበረ ቅዱሳን መጥቶ አባል ቤተ ክርስቲያንን የበለጠ ለማገልገልና አባቶቻችንን ለማገዝ ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም የቤተ ክርስቲያንን ክፍተት እሞላለሁ፤ አግዛለሁ ብሎ የተመሠረተ በመሆኑ ካለው የተማረ የሰው ኃይል አንጻር ሙያዊ ሥራዎችን ይሠራል፡፡ መሥራትም አለበት፡፡ ከዚህ በፊትም በተለይ በምህንድስናው ዘርፍ ዘርፈ ብዙ ሥራዎችን በመስራት ከፍተኛ የሆነ ወጭን ቤተክርስቲያኗ አንዳታወጣ አድርጓል፡፡ አባለቱም የማኅበረ ቅዱሳን አባል ስለሆኑ አያገባቸውም፤ አይመለከታቸውም ሊባል አይችልም፡፡ አባላት የቤተ ክርስቲያን ልጆች መሆናቸው መዘንጋት የለበትም፡፡ ስለሆነም አባላቱ በየአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ተመዝግበው ማገልገል እንዲሁም ማኅበሩ በሚያዛቸው ሁሉ መትጋት ይጠበቅባቸዋል፡፡ እያገለገሉም ነው፡፡

እየተነሱ ያሉት ተቃውሞዎች ጥናቱ ላይ ነው ወይስ ማኅበሩ ላይ ነው?
አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ፡- ጥናቱን አስመልክቶ ለተለያዩ የቤተ ክርስቲያኒቱ አካላት ገለጻ በማድረግ ውይይት ተካሒዶበታል፡፡ በዚህም ወቅት በጥናቱ ላይ የቀረቡ ትችቶች አሉ፡፡ ገንቢ አስተያየቶችም ተሰጥተዋል፡፡ ይህ እንግዲህ ተገቢ እና ጤናማ ነው፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ጥናቱ ይቅር ብለው የሚንቀሳቀሱ አካላት መነሳታቸውን ሰምተናል፡፡ ተቃውሟቸው ይሄ ችግር አለበት፤ ያ ደግሞ ቢስተካከል ጥሩ ነው በሚል አይደለም፡፡ ሰነዱ ላይ ያቀረቡት ክፍተት የለም፡፡ ተቃውሟቸው ጥናቱ ላይ ሳይሆን አዘጋጀው ብለው በሚያስቡት ማኅበረ ቅዱሳን ላይ ነው፡፡ እነዚህ ጥቂት አካላት በማኅበሩ ላይ የተለያዩ ትችቶችና የስም የማጥፋት ዘመቻ እያካሄዱ ነው፡፡ ይህ ሥህተትም ወንጀልም ነው፡፡ ጥናቱን ካዘጋጁት ባለሙያዎች መካከል የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ቢገኙበትም የተመረጡት በየአጥቢያቸው ባላቸው የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መነሻነት ነው፡፡ ትችቱም ሆነ ስም ማጥፋቱ ማኅበሩ ላይ ነው፡፡ ይህ ተገቢ ነው ብለን አናስብም፡፡ ጥናቱ ላይ አያስኬድም፤ ይህ ግድፈት አለበት ብለው ያቀረቡት ነገር የለም፡፡

ከጥናቱ ጋር በተያያዘ የማኅበሩን ስም የሚያጠፉና የተለያዩ ቅስቀሳዎችን የሚያደርጉ አሉና ከማኅበሩ ምን ይጠበቃል?
አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ፡- እንዲህ ያሉ ትችቶች መስመራቸውን የለቀቁ ናቸው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ተጠይቆ ያዘጋጀው ጥናት እንዳልሆነ ገልጸናል፡፡ እንቃወማለን የሚሉ ሰዎች በሰነዱ ላይ ምንም ዓይነት ትችት እያቀረቡ አይደለም፡፡ በሰነዱ ላይ ትችት የሚያቀርብ ሰው ሀሳቡ ጠቃሚ ቢሆንም ባይሆንም ለቤተ ክርስቲያን ጠቃሚ ነገር እንዳደረገ ይቆጠራል፡፡ አንድ ሰነድ በሆነ አካል ሊዘጋጅ ይችላል፡፡ በሚመለከታቸው አካላትም ይተቻል፤ ይታሻል፤ ከዚያ በኋላ ተግባራዊ ይደረጋል፡፡ እንዲህ ሲሆን ሰነዱ ሙሉ ይሆናል፡፡ ተግባራዊ ለማድረግም አያስቸግርም፡፡

እንቃወማለን የሚሉት አካላት ተቃውሟቸው ሰነዱ ላይ ሳይሆን አዘጋጀ ብለው የሚያስቡትንማኅበረ ቅዱሳንን ነው:: እነዚህ አካላት የተለየ ዓላማ ይዘው እየተንቀሳቀሱ ነው ብሎ መደምደም ይቻላል፡፡ ለቤተ ክርስቲያን ጥሩ አገልግሎት እየሰጠ ያለን ማኅበር ያለ ምንም ማስረጃ መተቸት አግባብ ነው ብለን አናምንም፡፡ እነዚህ አካላት የተለየ አጀንዳ ከሌላቸው በስተቀር ለቤተ ክርስቲያናችን የሚጠቅም ሰነድን ዝም ብሎ ገንቢ ባልሆነ መልኩ መቃወም ተገቢ አይደለም፡፡
ማኅበሩ እነዚህን አካላት አባቶች እንዲያርሟቸውና እንዲያስተካክሏቸው ይጠይቃል፡፡ ከዚህ በላይ እየገፋ ከሔደ በሕግ ይጠይቃል፡፡ ምክንያቱም በማኅበሩ ላይ ከፍተኛ የስም ማጥፋት ወንጀል እየፈጸሙ ናቸው፡፡ ከሁሉም በፊት አባቶቻችን እና የሚመለከታቸው አካላት እነዚህን ሰዎች ትክክለኛ አቋም እንዲይዙ አስፈላጊውን ሁሉ ያደርጋሉ ብለን እናምናለን፡፡

ጥናቱ ተግባራዊ እንዲደረግ የማኅበሩ ሱታፌ ምን ሊሆን ይችላል?
አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ፡- ሰነዱን ተግባራዊ የሚያደርገው በባለቤትነት ያዘጋጀው የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ነው፡፡ ይህንን የአሠራርና የአደረጃጀት ለውጥ ባለቤትም ሀገረ ስብከቱ ስለሆነ የሚያስፈጽመውም ራሱ ነው፡፡ መመሪያው ተግባራዊ እንዲሆን ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡ ቅዱስ ፓትርያርኩም በተደጋጋሚ አቅጣጫ ሰጥተውበታል፡፡ ማኅበራችንም የሚታዘዘውን የመሥራት ግዴታ አለበት፡፡ ሙያዊ በሆኑ ጉዳዮች ላይ በአባቶች አሳሳቢነት አግዝ፤ ፈጽም ሲባል አልችልም ማለት አይችልም፡፡ ለውጥ እንዲሁ በቀላሉ አይመጣም፡፡ ብዙ ተቃውሞዎች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ተቃውሞው በርትቶ የተጀመሩት የአሠራር ለውጦች ወረቀት ላይ ሰፍረው እንዳይቀሩ ማኅበሩ በአባቶች የሚታዘዘውንና የሚጠየቀውን ሁሉ ለመተግበር ዝግጁ ነው፡፡

 

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት መዋቅራዊ ለውጥ ረቂቅ ተፈጻሚ እንዲሆን ተጠየቀ፡፡

 ጥር 3/2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

– “ወደ ኋላ የምንመለስበት ምንም ምክንያት የለንም” /ቅዱስ ፓትርያርኩ/

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት መዋቅራዊ ለውጥ ረቂቅ ደንብ ተፈጻሚ እንዲሆን ከአዲስ አበባ አድባራትና ገዳማት የተውጣጡ አስተዳዳሪዎች፣ ጸሐፊዎች የሰበካ ጉባኤ ተወካዮች፣ የሰንበት ት/ቤቶት ተወካዮችና ምእመናን ጥር 2 ቀን 2006 ዓ.ም ከቀትር በኋላ ቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በቅዱስ ፓትርያርኩ ልዩ ጽ/ቤት በመገኘት ድጋፋቸውን ገለጹ፡፡

ድጋፋቸውን የገለጹት የቤተ ክርስቲያኒቷ ተወካዮች፤ ረቂቁ ተግባራዊ ሆኖ ቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ እድገት የምታሳይበትን ቀን እየናፈቅን ሳለ አንዳንድ አካላት ከቀናት በፊት “ረቂቅ ደንቡን ያዘጋጀው ማኅበረ ቅዱሳን ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ያወጣውን ደንብ አንቀበልም!” በማለት ደንቡ ተፈጻሚ እንዳይሆን፣ እንዲሁም ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የቅዱስ ፓትርያርኩ ረዳት የአዲስ አበባና የጅማ አኅጉረ ስብከት ሊቀጳጳስን በመዝለፍ ያቀረቡትን ጥያቄ ተቃውመዋል፡፡

“ቅዱስ አባታችን ያለፈው መነቃቀፍ ይበቃል፣ በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ላይ የሚደረግ የስም ማጥፋት ዘመቻና ሰድቦ ለሰዳቢ አሳልፎ መስጠት ሕገወጥ ተግባር መቆም አለበት፡፡” ያሉት እነዚሁ አካላት ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትና ለቅዱስነታቸው ሥራ መሣካት ወሳኝ አባት መሆናቸውን በመግለጽ የጀመሩትን የልማት፣ የመልካም አስተዳደር እንዲሁም የአቅም ግንባታና የአሠራር መርሕ ዕቅድ ማሣካት እንዲችሉ ድጋፍ እንዲደረግላቸው ጠይቀዋል፡፡

በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት መልካም አስተዳደርን ለማስፈን የሥራ አደረጃጀቱን ተግባራዊ ለማድረግና ከሕዝቡ የሚገኘውን አስራት በኩራቱን፣ መብዓውንና በልማት ዘርፎች የሚገኘውን ገቢ በአግባቡ ጥቅም ላይ ለማዋል፣ የሒሳብ አጠቃቀምን ከወቅቱ ሥልጣኔ ጋር አዛምዶ አለማቀፋዊነቱን ጠብቆ መሥራት፣ ስብከተ ወንጌልን በተገቢው ሁኔታ ማዳረስ ወቅቱ የሚጠይቀው ሁኔታ በመሆኑ የአዲስ አበባ አድባራትና ገዳማት ተወካዮች እቅዱ ተግባራዊ እንዲሆን ድጋፋቸውን ሰጥተዋል፡፡

ቅዱስነታቸው በሰጡት ምላሽም “ባለፈው ጊዜ የመጡትም ሆነ ዛሬ የመጣችሁት እናንተም ሁላችሁም የቤተ ክርስቲያን ልጆች ናችሁ፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን የምትመሩ፣ የምታስተዳድሩና ምእመናንን የምታስተምሩ ናችሁ፡፡ ሁላችሁም ልጆቻችን ስለሆናችሁ አስተናግደናችኋል፡፡ በእኩልነት የሁሉንም ሀሣብ መስማትና ከፍጻሜ የማድረስ ኃላፊነት አለብን” ብለዋል፡፡

ቅዱስነታቸው በመቀጠልም “ከቀናት በፊት የመጡት ገንቢና ተገቢ ያልሆነ አነጋገር ተናግረዋል፡፡ አግባብ ያልሆነ አነጋገር ማንም አይወድም፡፡ በሥነሥርዓት፣ በግብረገብነት፣ በቤተ ክርስቲያን ሰውነት፣ በእርጋታና በሰከነ አዕምሮ መነጋገር ትልቅ ነገር ነው፡፡ ንግግራችን ሁልጊዜ ቤተ ክርስቲያንን ያማከለ መሆን አለበት፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን ሕልውና ይቀድማል፡፡ እናንተ ያቀረባችሁበት መንገድ የሚያስመሰግናችሁ ነው፡፡ የሰከነ መንፈስ ይታያል፡፡ በቀረበው ጥናት ላይ ሊቃውንቱ ይጨመሩበት የሚል ሀሳብ ስለቀረበም ከ9-11 አባላት ያሉት ኮሚቴ ተቋቁሞ ሥራውን ለመሥራት ዝግጅት ላይ ነው፡፡ ወደኋላ የምንመለስበት ምንም ምክንያት የለንም፡፡ መስመሩም አይለወጥም፡፡ በታቀደው መሠረት ቤተ ክርስቲያኒቱ ቀናና መልካም እንዲሁም ተጠያቂነት ያለው አስተዳደር እንዲኖራት ነው ጥረታችን$፡፡ በማለት ለተወካዮቹ ገልጸዋል፡፡

ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የተውጣጡ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች፣ የልዩ ልዩ ክፍፍ አገልጋዮች፣ የሰበካ ጉባኤና የሰንበት ት/ቤቶች ተወካዮች ረቂቅ ህገ ደንቡን በመደገፍ ያዘጋጁትን የአቋም መግለጫና ያሰባሰቡትን ፊርማ ለቅዱስነታቸው አስረክበዋል፡፡

 

christmas 1

በድንግልናሃ ንጹሕ እግዚአብሔር ተወልደ

 ታኅሣሥ 26 ቀን 2006 ዓ.ም.

መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

christmas 1
በፈቃደ አቡሁ ወረደ፣ኀበ ማርያም ተአንገደ፤ በድንግልናሃ ንጹሕ እግዚአብሔር ተወልደ። በጎለ እንስሳ ተወድየ፣ አምኃ ንግሡ ተወፈየ፤ ወከመ ሕጻናት በከየ፣ እንዘ ይስእል እምአጥባተ እሙ ሲሳየ።

በአባቱ ፈቃድ ወረደ፣ በማርያም ዘንድ፣ እንግዳ ሆነ፣ እግዚአብሔር በንጹሕ ድንግልናዋ ተወለደ። በእንስሳት በረት ተጨመረ፣ የንግሡንም እጅ መንሻ፡ ተቀበለ፣ ከእናቱ ጡቶች ምግብን እየለመነ እንደ ሕጻናት አለቀሰ። (ቅዳሴ ዲዮስቆሮስ)
እግዚአብሔር አምላክ ዓለምንና በውስጧ ያሉትን ፈጠረ ሌሎች ፍጥረታት ለአንክሮ ለተዘክሮ ሲፈጠሩ ሰውና መላእክት ግን ፍቅሩን ክብሩን ይወርሱ ዘንድ ተፈጠሩ፡፡ ዘፍ 1፡1

የሰው ልጅን /አዳምን/ ፈጥሮ የሚያስፈልገውን አዘጋጅቶ፣ ዕውቀትንና ሥልጣን ሰጥቶ፣ በጸጋ አምላክነትን ሾሞ ፣መመሪያ ሰጥቶ፣ በክበር እንዲኖር ፈቀደለት ፡፡ በመጀመሪያው ዕለትና ሰዓት ከተፈጠሩት መላእክት መካከል በክብር ይልቅ የነበረው ሳጥናኤል /የኋላ ስሙ ዲያብሎስ / አምላከነት በመሻቱ ተወርዶ ሳለ አዳምንም በተዋረደበት ምኞትና ፍላጎት እንዲወድቅ ክብሩን እንዲያጣ ከአምላኩም እንዲለይ አደረገው፤ እግዚአብሔርን፣ ጸጋውን፣ ሹመቱን፣ ወዘተ አጣ /ኃጥአ/፡፡ ኃጢአት የሚለው ጽንሰ ሐሳብ ከዚህ የተወሰደ ነው፡፡

አዳም ከእግዚአብሔር በመለየቱና ክብሩን በማጣቱ ተጸጽቶ ንሰሐ ገባ ፡፡ ሥርየተ ኃጢአት የሚሆን መስዋእትም በማቅረቡ፤ እግዚአብሔር አምላክ ልመናውንና መስዋእቱን ተቀብሎ እርሱንና ዘሩን ለማዳን እንደሚመጣ ቃል ኪዳን ገባለት “መልዓትንና ዓመታትን በዚህ ምድር ላይ ሠራሁልህ፡፡ ይኸውም እነርሱ እስኪፈጸሙ ድረስ በምድር ላይ ትኖርና ትመላለስ ዘንድ ነው፡፡ የፈጠረችህና የተላለፍካት ከገነት ያወጣችህና በወደቅህም ጊዜ ያነሳችህ ዳግመኛም አምስት ቀን ተኩል ሲፈጸም የምታድንህ ቃሌን እልክልሃለሁ” /ገድለ አዳም/ ብሎ እግዚአብሔር ለአዳም ነገረው፡፡ አዳምም አምስት ቀን ተኩል የሚለውን ቃል ከእግዚአብሔር በሰማ ጊዜ የእነዚህን ታላላቅ ነገሮች ትርጓሜ ሊያስተውል አልቻለም፡፡ ስለዚህም እግዚአብሔር አምስት ቀን ተኩል ማለት አምስት ሺህ አምስት መቶ ዓመታት መሆናቸውን ገልጾ አርአያውና አምሳያው ለሆነው አዳም በቸርነቱ ተርጎመለት፡፡ እርሱንና ዘሩን ለማዳን እንደሚመጣ ተስፋ ሰጠው፡፡ ዘፍ 2፡7 ፣ሔኖክ 19 ፡19 ፣ ኩፋሌ 5፡6

አዳምም ይህንን ተስፋ ለልጆቹ አስተማራቸው፤ ልጆቹም ተስፋው የሚፈጸምበትን ጊዜ ለማወቅ በፀሐይ፣ በጨረቃና በክዋክብት /ዛሬም ቤተክርስቲያናችን ይህንን አቆጣጠር ትጠቀምበታለች/ ዘመናትን እየቆጠሩ “ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንኃለሁ” ያለውን የአዳኝ ጌታ መወለድን ነብያት ትንቢት እየተናገሩ፤ አበውም ሱባኤ እየገቡ ተስፋውን ይጠብቁ ነበር፡፡ ከነሱም ውስጥ:-

1. ሱባኤ ሔኖክ

ሔኖክ ሱባኤውን ሲቆጥር የነበረው በአበው ትውልድ ሲሆን ሰባቱን መቶ ዓመት አንድ እያለ ቆጥሯል። በስምንተኛው ሱባኤ ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሚወለድ ትንቢት ተናግሯል። አቆጣጠሩም ከአዳም ጀምሮ ነው። 8×700=5600ዓመት ይሆናል። 5500ዓመተ ዓለም ሲፈጸም ኢየሱስ ክርስቶስ እንደተወለደ ያጠይቃል።

ትንቢቱም እንዲህ ይላል። “ስምንተኛይቱ ሰንበት ጽድቅና ኩነኔ የሚታወቅባት ሰባኤ ናት፡፡ ሰይፍም ለርሰዋ ይሰጣታል፤ ታላቁ ንጉሥ የሚመሰገንበት ቤትም በርሰዋ ይሰራል፡፡ ምሥጋናውም ዘላለማዊ ነው፡፡” ሔኖክ 35፡ 1-2 ክፍል 91 በማለት ሲተነብይ መተርጉማን እንዲህ ይመልሱታል፡፡ ለርሰዋ ሰይፍ ይሰጣታል ማለቱ፤ ጸድቅና ኩነኔ የሚታወቅበት ወንጌል ያን ጊዜ በዓለም ሁሉ ትሰበካለች ማለት ነው፡፡ የታላቁን ንጉሥ ቤት ይሠራል ማለቱ፤ የነገሥታት ንጉሥ ኢየሱስ ክርስቱስ የሚመሰገንበት ቤተክርስቲያን ትሰራለች ማለት ነው፡፡ ምስጋናውም ዘላለማዊ ነው ማለቱ፤ ሰውና መላእክት በአንድነት ሆነው “ሰብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር” እያሉ ዘወትር ያመሰግናሉ ማለት ሲሆን ስምንተኛይቱ ሰንበት ለክርስቲያኖች የተሰጠችበትን ዕለት ልደት ክርስቶስ ናት ይሏታል፡፡

2 ሱባኤ ዳንኤል

yeledeteስለ ጌታችን ሰው መሆን ጊዜ ወስኖ ሱባኤ ቆጥሮ የተናገረው ዳንኤል ነው፡፡ የዳንኤል ሱባኤ የሚቆጠረው በዓመት ነው ፡፡ ዳንኤል 70ው ዘመን በተፈጸመ ጊዜ እጐበኛችኋለሁ ተብሎ በኤርምያስ የተገረውን ትንቢት እያስታወስ ሲጸልይ መልአኩ ቅ/ገብርኤል በሰው አምሳል ተገልጾ እንዲህ ብሎታል፡፡ “እግዚአብሔር ልምናህን ሰምቶሃልና እነግርህ ዘንድ መጥቻለሁ፡፡ አሁንም ነገሩን መርምር ራእዩንም አስተዋሉ ኅጢአት የሚሰረይበትን ቅዱሰ ቅዱሳን ጌታም የባህርይ ክብሩን ገንዘብ የሚያደርግበት ሰባው ሱባኤ ሊደርስ ሊፈጸም ነው ብለህ ወገኖችህን ቅጠራቸው ብሎታል፡፡” /ዳን 9፡22- 25 ኤር 29፡1ዐ/

ሰባ ሱባኤ አራት መቶ ዘጠና ዓመት ነው /7ዐX7= 490/ ይህ ጊዜ ከሚጠት እስከ ክርስቶስ መምጣት ያለው ጊዜ ነው /ትርጓሜ ሕዝ፡4፡6/

3. ሱባኤ ኤርምያስ

ኤርምያስ ከባቢሎን እንደተመለሰ በፈረሰው ቤተ መቅደስ ውሰጥ ሆኖ ሲጸልይ ሳለ ራዕይ አየ በሦስተኛው ቀንም እንዲህ ብሎ ትንቢት ተናገረ፡፡ “ፈጣሪያችንን በአንድ ቃሉ አመሰግኑ የአብ የባሕርይ ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስን አመስግኑ ከዚህ በኋላ ሰው ሊሆን ሥጋ ሊለብስ ወደዚህ ዓለም ሊመጣ የቀረው 333 ሱባኤ ዕለት ነውና እርሱ ወደዚህ ዓለም ይመጣል፡፡ አሥራ ሁለት ሐዋርያትንም ይመርጣል…፡፡” ተረፈ ኤር 11፤37 ፣38፣42-48፡፡ ኤርምያስ ሱባኤውን የጀመረበትን ትንቢቱን የተናገረበት ራእዩን ያየበት ዘመን ዓለም በተፈጠረ 5054 ዓመት ነው፡፡ ስለዚህ ትንቢቱ ከተነገረበት እስከ ክርስቶስ ልደት ያለው ጊዜ 446 ዓመት ነው፡፡

ይኸውም በኤርምያስ ሱባኤ አንዱ 49ዐ ዕለት ነው መላው ሱባኤ 49ዐX333 = 163,170 ዕለት ሲሆን ወደ ዓመት ሲለወጥ 163, 170÷365 =446 ዓመት

ኤርምያስ ሱባኤውን መቁጥር የጀመረበት ዘመን …….. 5ዐ54 ዓመተ ዓለም

ትንቢቱ ከተነገረበት ዓመት እስከ ክርስቶስ ልደት ……. 446 ዓመት

በተነገረው ትንቢት በተቆጠረው ሱባኤ መሠረት 55ዐዐ ዓመት ሲፈጸም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቱስ መወለዱ በዚህ ይታወቃል፡፡

4. ዓመተ ዓለም

የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱሳት መጻሕፍትን መርምረው ሱባኤያትንና ሰንበታትን አውቀው ከአዳም እስከ ክርስቶስ ያለውን ዘመን ቁጥር 55ዐዐ ዓመት መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡

ይኸውም ከአዳም አስከ ኖኅ …… 2256 ዓመት

ከኖኅ እስክ ሙሴ ……… 1588 ዓመት

ከሙሴ እስከ ሰሎሞን …. 593 ዓመት

ከሰሎሞን አስከ ክርስቶስ 1063 ዓመት

                        55ዐዐ ዓመት

ጌታችን ኢየሱስ በተነገረው ትንቢት፤ በተቆጠረው ሱባኤ መሠረት /ዓመተ ዓለም፣ ዓመተ ኩነኔ ፣ዓመተ ፍዳ/ አምስት ቀን ተኩል / 55ዐዐ ዓመት/ ሲፈጸም /በእግዚአሔር ዘንድ 1ዐዐዐ ቀን እንደ አንድ ቀን ናት፡፡ 2ኛ ጴጥ. 3፤8 / በ5501 ዓመት ማክሰኞ ታኀሣሥ 29 ቀን ተወለደ፡፡

“ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ሥምረቱ ለሰብእ” አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ የዘመኑ ፍጻሜ /የገባው ቃል ኪዳን፣ የተነገረው ትንቢት፣ የተቆጠረው ሱባዔ/ ሲደርስ ከእመቤታችን ከቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም ያጣነውን ልጅነት ሊመልስልን፣ ከተቀማነው ርስት ሊያስገባን፣ የገባንበትን እዳ ሊከፍልልን ተወለደ፡፡

የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት ተወለደ ፡፡ ገላ 4፣4 እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ፤ ቅዱስ ኤፍሬምም “ ቅድስት ድንግል ማርያም ፍጥረታትን ያስገኘ፤ የነገሥታት ንጉሥ የሆነውን ዳግማዊ አዳም ኢየሱስ ክርስቶስን ወለደችልን፡፡ የአሮን በትር ለምልማና ፍሬ አፍርታ ተገኝታ ነበር፤ ይህም ክርስቶስ በድንግልና የመወለዱ ምሳሌ ነው፡፡ እጹብ ድንቅ የሆነ ልደት በዛሬዋ ቀን እውን ሆነ፡፡ ድንግል የሆነችው ቅድስት ማርያም በድንግልና ጌታችንን መድኃኒታችንን ወለደችልን፡፡” ብሏል፡፡

“የእሥራኤል እረኛ ሆይ አድምጥ … በኪሩቤል ላይ የምትቀመጥ ተገለጥ” ብሎ የለመነዉ የዳዊት ልመና በእዉነት ተፈጸመ፡፡ መዝ 70፥1። የእስራኤል እረኛ፤ በእረኞች መካከል በከብቶች በረት ተወለደ። ሉቃ 2፥7፡፡ እረኞች ለእረኛቸው ዘመሩ፤ ላሞች፣ በጎችና አህዮች በበረት የተኛውን ሕፃን በትንፋሻቸው አሟሟቁ። በኦሪት ድንኳን በሙሴ ሕግ መሠረት ለመሥዋዕት ይቀርቡ የነበሩ እንስሳት በልደቱ ደስ ተሰኙ፤ የነርሱን መሥዋዕት የሚያስቀር አማናዊው የእግዚአብሔር በግ ተወልዷልና።

ለሰው ሁሉ ብርሃን የሚሰጥ እግዚአብሔር በጨለማው ዓለማችን ተወለደ። (ዮሐ.1፥9-14) ነቢያትና መምህራን ጠፍተውባት፣ የኃጢአት ጨለማ ዉጧት፣ በድንቁርና ባሕር ውስጥ ሰጥማ በነበረችው የሰው ልጆች ዓለም የእውነት ፀሐይ ወጣ። እነሆ ይህን ይገልጥ ዘንድ መድኅን በእኩለ ሌሊት በጨለማ ተወለደ፤ በተወለደ ጊዜ ግን ክብሩ በዙርያው አበራ። (ሉቃ.2፥8-9)

ለመንግሥቱ ወርቅ ተገበረለት። ኃያል መንግሥቱን ግን በምድር ላይ በትህትና ነበር የገለጣት፤ በከብቶች በረት በመወለድና በአህያ ውርንጭላ ተቀምጦ በመሄድ። (ሉቃ.19፥28-38) የአባታችን የዳዊት መንግሥት ያለልክ ከፍ ከፍ አለች፤ እግዚአብሔር ሰው ሆኖ የዳዊት ልጅ ሆኗልና። ቅዱስ ገብርኤል ቅድስት ድንግል ማርያምን ባበሠራት ጊዜ “እርሱ ታላቅ ይሆናል፣ የልዑል ልጅም ይባላል፤ጌታ አምላክም የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል፣ በያዕቆብ ቤትም ላይ ለዘላለም ይነግሣል፣ ለመንግሥቱም መጨረሻ የለዉም” ብሎ የተናገረዉ ዛሬ ተፈጸመ፡፡ (ሉቃ.1፥32)፡፡

በባሕርይው የፍጥረት ሁሉ ገዥ የሆነዉ የእግዚአብሔር ልጅ ከዳዊት ልጅ ሥጋን ነስቶ ሰዉ በሆነ ጊዜ የአባቱን የዳዊትን ዙፋን እስከ ጽርሐ አርያም ድረስ ከፍ ከፍ አደረጋት። እነሆ ንጉሥ ክርስቶስ በያዕቆብ ቤት (በምእመናን) ላይ ለዘላለም ነገሠ። ለመንግሥቱ የአሕዛብ ነገሥታት ተገዙላት፤ የእግዚአብሔር መንግሥት ናትና ፍጥረታት ሁሉ ይገዙላታል። (ኤር.23፥5)

ለክህነቱ ዕጣን ተሰጠው። ክህነቱም የአበውን እና የሌዋውያንን ክህነት የምትፈጽም የዘላለም ሰማያዊት ሥራው ናት። እነሆ የአብ ሊቀ ካህናት እርሱ የሰውን ባሕርይ ከራሱ ጋር አስማማ። ራሱ ካህን፣ ራሱ መሥዋዕት፣ ራሱ ተቀባይ ሆኖ የፈጸማት የክህነት ሥራው የዘላለም ድኅነትን አስገኘች።

ለሞቱ ከርቤ ቀረበለት። እነሆ እግዚአብሔር ሰው የሆነበት ዋናው ምክንያት በሞቱ ሞትን ድል ለመንሣት ነውና በልደቱ ሞቱ ተሰበከ። ከርቤ ለሞቱ ሲቀርብለት የማይሞተው እርሱ ለሰው ልጆች ሲል የሚሞት ሥጋን እንደለበሰ ታወቀ።

የአሕዛብ ነገሥታት ወርቅ ገበሩለት፤ ምእመናን ደግሞ ጽሩይ፣ ንጹሕ፣ ሰማያዊ የሆነ ልቦናን እና እምነትን ለእርሱ እናቀርባለን። (1ኛ ጴጥ.1፥6) ሰብአ ሰገል ራሱ የፈጠረውን ወርቅ ገበሩለት፤ እኛም በርሱ ጸጋና ሥራ ያገኘነውን ንጹሕና ሰማያዊ እምነታችንን እናቀርብለታለን (ይሁ.3)።

ነገሥታቱ ዕጣን ገበሩለት፤ ምእመናን ደግሞ ቂም በቀል የሌለበትን፣ ከመልካም እና ከንጹሕ ልብ የሚወጣ የምስጋና ጸሎት እናቀርባለን፤ “ጸሎቴን በፊትህ እንደ ዕጣን ተቀበልልኝ፥ እጅ መንሣቴንም እንደ ሠርክ መሥዋዕት ትሁን።” እንዳለ ንጉሥ ዳዊት (መዝ.140፥2) ።

ስለሰው ልጆች ፍቅር ሲል ለሚቀበለው ሞት ከርቤ ገበሩለት፤ ምእመናን ደግሞ ለእግዚአብሔርና ለሰው ልጆች ያለንን ፍቅር ለእርሱ እናቀርባለን። ነገሥታቱ እርሱ ከፈጠረው ከርቤ ወስደው እጅ መንሻ አቀረቡ፡፡ ምእመናን ደግሞ ከእርሱ ከተማርነው፣ ከመንፈስ ቅዱስ ጸጋ ከተቀበልነው ፍቅር መልሰን ለእርሱ እናቀርባለን። “እርሱ ስለኛ ነፍሱን አሳልፎ ሰጥቷልና በዚህ ፍቅርን አውቀናል፤ እኛም ስለ ወንድሞቻችን ነፍሳችንን አሳልፈን ልንሰጥ ይገባናል፡፡ (1ኛ ዮሐ.3፥16)።”

ነቢዩ ኢሳይያስ “በጨለማ የሄደ ሕዝብ ብርሃን አየ በሞት ጥላ አገርም ለኖሩ ብርሃን ወጣላቸዉ” ብሎ የተናገረዉ ትንቢት ተፈጸመ (ኢሳ.9፥2)። የቅድስናዉ ተራራና ማደሪያው ወደ ሆነች ወደ መንግሥተ ሰማያት ይወስደናል፡፡ በዚች የዘላለም ሃገራችንም የሚያበራልን ፀሐያችን እርሱ ነዉ፡፡ (ራእይ.21፥23)።

እነሆ ሰው የመሆኑ ዜና የሰው ልጆች ሁሉ ደስታ ነው፡፡ “እነሆ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ፡፡ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋልና።” የሚል ዜና በሰማያውያን መላእክት ተሰበከ። (ለቃ.2፥11)

የምድር ኃያላን ነገሥታት በከብቶች በረት ውስጥ በጨርቅ ተጠቅልሎ ለተኛው ሕፃን መብዓ አቀረቡ። ንጹሐንና ኃያላን የሚሆኑ የሰማይ መላእክት ደግሞ እግዚአብሔር ለሰው ፍቅር ሲል እንደ ሕፃን ተጠቅልሎ ሲያዩ በታላቅ ትሕትና ከእረኞች ጋር ዘመሩ። (ሉቃ.2፥13)

በዳዊት ከተማ በቤተልሔም ድንቅ ነገር ተደረገ። ዳዊት በወርቅ ያጌጠ የተልባ እግር መጎናጸፊያ የለበሰባት ቤተልሔም የሰማይና የምድር ፈጣሪ በጨርቅ ተጠቅልሎ ተገኘባት። ቤተልሔም ከዳዊት ዘመን አብልጣ ከበረች፤ የእግዚአብሔር ክብር አብርቶባታልና፤ የልዑላን መላእክት ዝማሬ ተሰምቶባታልና። (ሚክ.5፥2)

በዚህች ዕለት እግዚአብሔር ወደ ኃጢአተኞች መጣ፤ ስለዚህ ጻድቁ በኃጢአተኞች ላይ አይታበይ፡፡ በዚህች ቀን የሁሉ ጌታ የሆነው እርሱ ወደ ባሮቹ መጣ፤ እናንተ ጌቶች ሆይ እንደ ጌታችን ለአገልጋዮቻችሁ ቸርነትን አድርጉላቸው፡፡ በዚህች ቀን ባለጠጋ የሆነው እርሱ ስለ እኛ ሲል ደሃ ሆነ፡፡ እናንተ ባለጠጎች ሆይ ከማዕዳችሁ ለድሃው አካፍሉ፡፡ በዚህች ቀን እኛ ያላሰብነውን ስጦታ ከጌታ ዘንድ ተቀበልን፤ እኛም ምጽዋትን ለሚጠይቁን ድሆች ቸርነትን እናድርግ፡፡ ከእኛ ይቅርታን ሽተው የመጡትን ይቅር እንበላቸው፡፡ በዛሬዋ ቀን የፍጥረት ጌታ የሆነው እርሱ ከባሕርይው ውጪ የሰውን ተፈጥሮ ገንዘቡ አድርጎ በሥጋ ተገልጦአልና፣ እኛም ወደ ክፉ ፈቃድ የሚወስደንን ዐመፃ ከእኛ ዘንድ አርቀን በአዲስና እርሱ በሰጠን መንፈሳዊ ተፈጥሮ እንኑር፡፡… እኛ በአምላክ ማኅተም እንድንታተም እርሱ አምላክነቱን ከእኛ በነሳው ሥጋ አተመው፡፡…ሰው አምላክ ሆነ አምላክ ሰው ሆነ ማለት ነው፡፡

የአምላካችንን የኢየሱስ ክርስቶስን የልደት በዓል ስናከብር ፍቅሩን እያሰብን በኃጢያታችን ምክንያት ከልባችን ያወጣነው ሁሉ ዛሬም በልባችን እንዲወለድ ያስፈልጋል፡፡ “የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ የት አለ?” ማቴ. 2÷1
እግዚአብሔር ለምን ሰው ሆነ?

ከንጹሕ ባሕርይ ተፈጥሮ የእግዚአብሔር ልጅ ሆኖ በደስታ ይኖር የነበረ ሰው የፈጣሪውን ትዕዛዝ በመተላለፉ ከንጽህና ወጥቶ ኃጢአትን ለበሰ:: ሕይወቱን አስወስዶ ሞትን ተቀበለ:: የእግዚአብሔር ልጅነቱን አስቀርቶ የዲያቢሎስ ምርኮ ሆነ:: ደስታውን አጥቶ ኃዘን አገኘው:: ተጸጽቶ የጥንት ሕይወቱንና ደስታውን ለማግኘት ጥረት ቢያደርግም፤ ንጹህ ባሕርይው ስላደፈበት የሞት ፍርድን ሊያስቀርለት አልቻለም::

ዳግማዊ አዳም የተባለ የፍቅር አምላክ፣ የሁሉ ፈጣሪ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን የሞት ፍርድን ሊያስቀር ኃጢአትን ደምስሶ ከሞት ፍርድና ከገሃነም ነጻ ሊያወጣ ዘር ምክንያት ሳይሆነው ሰው ሆነ፤ ተወለደ:: “እርሱም ኃጢአትን ሊያስወግድ እንደ ተገለጠ ታውቃላችሁ፥ በእርሱም ኃጢአት የለም።” 1ዮሐ 3:5

በዚህም መሰረት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር በአምስት ሺህ አምስት መቶ ዓመተ ዓለም ዘመነ ዮሐንስ መጋቢት ሀያ ዘጠኝ ቀን እሑድ ከቀኑ ሶስት ሰዓት ተጸነሰ:: በአምስት ሺህ አምስት መቶ አንድ ዓመተ ዓለም በዘመነ ማቴዎስ ታኅሣሥ ሃያ ዘጠኝ ማክሰኞ ከሌሊቱ አስር ሰዓት ተወለደ::

ገናና የገና ጨዋታ

ገና-ጌና-ገኒን-ገነ፤ልደት

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደበት ቀን በዓል ገና ወይም በዓለ ልደት በመባል ይታወቃል:: ገና የሚለው ቃል ገነወ አመለከ ከሚለው የግእዝ ቃል የተወሰደ ነው:: የጌታችን ልደትም የአምላክ ሰው፤ ሰው አምላክ የመሆን ምሥጢር የተገለጠበት ታላቅና ገናና ስለሆነ ገና ተብሏል:: አምላክ አለምን ከፈጠረበት ጥበቡ ዓለምን ያዳነበት ጥበቡ ይበልጣል እንዲል ሃይማኖተ አበው::

የገና ጨዋታ

በሃገራችን በኢትዮጵያ የገና በዓል በተለያዩ ዝግጅቶች ደምቆ ይከበራል:: በተለይ በገጠሩ ያገራችን ክፍል ከዚህ በዓል ጋር በተያያዘ አባቶችና እናቶች ክብረ በዓሉን ምክንያት በማድረግ በገና ይደረድራሉ:: ወጣቶችም የገና ጨዋታ ይጫወታሉ:: “በገና” ስሙን ያገኘው በገና በዓል ወቅት የሚደረደር በመሆኑ ነው ሲሉ አንዳንድ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ያስተምራሉ:: በሌላም ትውፊት በተለይ በገጠሩ አካባቢ የሚገኙ ወጣቶችና አዛውንቶች የሚጫወቱት የገና ጨዋታ ራሱን የቻለ ባህልና ትውፊት አለው:: የገና ጨዋታ ራሱ በተቆለመመ በትርና ሩር የተባለ ከዛፍ ሥር በተሠራ ክብ እንጨት(ኳስ) እያጎኑ የሚጫወቱት ጨዋታ ነው፡፡

ሰብአ ሰገል በኮከብ እየተመሩ ወደ ቤተልሔም ሲሔዱ “የተወለደው የአይሁድ ንጉስ ወዴት አለ” በማለት ቢጠይቁ ይህንን አስደንጋጭ ጥያቄ የሰማው ንጉሥ ሔሮድስ “እኔ ንጉሥ ሆኜ ሳለሁ ሌላ ንጉሥ እንዴት ይወለዳል” በማለት የተወለደውን ንጉሥ ለመግደል አገልጋዮቹን ከሰብአ ሰገል ጋር ሄደው ቦታውን አይተው እንዲመለሱ ላካቸው፡፡ የሔሮድስ አገልጋዮች ከተቀላቀሉ በኋላ እየመራ ያመጣቸው ኮከብ ጌታ የተወለደበትን ቦታ መምራቱን አቆመ፡፡ ሰብአ ሰገል ተጨንቀው “የኮከቡ እርዳታ ለምን ተለየን” ብለው ሲመረምሩ ከነሱ ዓላማ ውጭ ሌላ ሀሳብና ተንኮል ይዘው የተገኙ ሰዎችን አገኙ፡፡ “በእናንተ ምክንያት የእግዚአብሔርን እርዳታ አጣን”፡፡ ብለው ሦስቱም ነገሥታት(ሰብአ ሰገል) ከአንዱ ወደ አንዱ እየተቀባበሉ በብትር እየመቱ አስወገዷቸው፡፡

ኮከቡም እየመራ ጌታ በተወለደበት ቦታ ቤተልሔም አደረሳቸው ከእረኞችና ከመላእክት ጋራ አመሰገኑት፡፡ እረኞች ጌታ በተወለደ ጊዜ ጨለማ ተሸንፎ አካባቢያቸው በብርሃን ተመልቶ መንፈስ ቅዱስ በገለጸላቸው ምስጢር ከመላእክት ጋራ “ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ሥምረቱ ለሰብእ” እያሉ ሲያመስግኑና ሲደሰቱ አድረዋል፡፡ በአሉ እረኞች ክብር ያገኙበት ምስጢር የተገለጠላቸው ስለሆነ በስነ ቃል “በገና ጨዋታ አይቆጡም ጌታ” እየተባለም በጨዋታ እንደሚከበር እንደሆነ አበው ይናገራሉ፡፡

ይህ ትውፊት የገና ጨዋታ እየተባለ ወጣቶች አዛውንቶች በጨዋታ ያከብሩታል፡፡ ራሱ የተቆለመመውና ሩሯን የሚያጎነው በትር የጌታችን ምሳሌ ሲሆን ሩሩ ደግሞ የሳጥናኤል ምሳሌ ነው:: ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን ዝቅ አድረጎ የሰውን ሥጋ በመልበስ ወደዚህ ምድር እንደመጣና በሩር የተመሰለውን ሰይጣንን እንደቀጠቀጠው የሚያሳይ ምሥጢር ያለው ጨዋታ ነው::

 

 

 

abuna m 2006

ቅዱስ ፓትርያርኩ ልደተ እግዚእን አስመልክቶ ቃለ ምዕዳን አስተላለፉ

ታኅሣሥ 25 ቀን 2006 ዓ.ም. 

 

abuna m 2006የ2006 ዓ.ም. የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት (ልደተ እግዚእ) በማስመልከት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ለመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን የእንኳን አደረሳችሁ ቃለ ምዕዳን አስተላለፉ፡፡

ቅዱስነታቸው ያስተላለፉትን ቃለ ምዕዳን ከዚህ በታች አቅርበነዋል፡፡

 lidt 2006 01lidt 2006 02

uk macele

የለንደን ደ/ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን እንደገና ተከፍታ አገልግሎት መስጠት ጀመረች

 ታኅሣሥ 25 ቀን 2006 ዓ.ም. 

 

ከUK ቀጠና ማዕከል

uk maceleየኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ካህናትን እና ምእመናንን ባሳዘነ ሁኔታ ከዘጠኝ ወራት በላይ ተዘግታ የቆየችው የለንደን ርእሰ አድባራት ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን እሁድ ታኅሣስ ፳ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም. የሰሜን ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ እንጦንስ በተገኙበት በይፋ እንደገና ተከፍታ አገልግሎት መስጠት ጀመረች።

ደብሩ እስካሁን በእንግሊዝ መንግሥት የሚታወቅበትን የእምነት እና የበጎ አድራጎት ተቋማት (Charity) ምዝገባ ወደ “ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ” (Company Limited by Guarantee) ምዝገባ ለመቀየር በተነሱ ሰዎች እና ይህ ምዝገባ ከቤተ ክርስቲያናችን ቃለ አዋዲ ጋር ስለማይስማማ፣ ኃላፊነቱንም በጥቂት ሰዎች እጅ ብቻ የሚያስገባና እነርሱም የሚኖርባቸውን ተጠያቂነት ስለሚቀንስ ለቤተ ክርስቲያን አይስማማም በማለት በተቃወሙ ወገኖች መካከል ልዩነት በመፈጠሩ እና ይህም አለመግባባት ተጠንክሮ መጋቢት ፩ ቀን ፳፻፭ ዓ.ም. ካህናት ጸሎተ ኪዳን አድርሰው ቅዳሴ ለመግባት እየተዘጋጁ በነበረበት ሰዓት ላይ በተነሳ ረብሻ ቤተ ክርስቲያኒቱ መዘጋቷ ይታወሳል።

ቅዱስ ሲኖዶስም ከሀገረ ስብከቱ በቀረበለት ጥያቄ መሠረት ብፁዕ አቡነ ገብርኤልንና ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስን በሚያዝያ ወር ወደ ለንደን በላከበት ወቅት ምንም እንኳን አብዛኛው የደብሩ ካህናት፣ የሰ/ት/ቤት ወጣቶች እና ምእመናን በቃለ አዋዲ እና በቅዱስ ሲኖዶስ መመሪያ እንደሚመሩ ቢያረጋግጡም (ከዚህ ቀደም የደብሩ አስተዳደር በሀገረ ስብከቱ ስር አልነበረም)፣ ጥቂት ካህናት እና የተወሰኑ ምእመናን ባለመስማማታቸው ሊቃነ ጳጳሳቱ ከአንድ ወር ቆይታ በኋላ ለቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ /ርክበ ካህናት/ ወደ አዲስ አበባ ተመልሰዋል።

በወርሀ ጥቅምት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እንጦንስ፣ በወቅቱ ከአኀት አብያተ ክርስቲያናት ጋር ለመወያየት ወደ እንግሊዝ መጥተው ከነበሩት ከብፁዕ አቡነ ገብርኤል እና ከብፁዕ አቡነ ያዕቆብ ጋር በመሆን ቤተ ክርስቲያኒቱ ተከፍታ አገልግሎት መስጠት እንድትጀምር ለማድረግ ቢሞክሩም መከፈቷን የሚቃወሙ ሰዎች በር ላይ ረብሻ በማስነሳታቸው ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳቱ ከፖሊስ ጋር በመነጋገር እና ለህዝቡ ደህንነት በመስጋት ለሌላ ጊዜ እንዲሸጋገር አድርገው ነበር።

ቤተ ክርስቲያኒቱ ከዘጠኝ ወራት በላይ በእንዲህ ያለ ሁኔታ አገልግሎት መስጠት ሳትችል ብትቆይም፣ አሁን ያለው የደብሩ ሰበካ ጉባኤ ከሀገረ ስብከቱ አስተዳደር ጉባኤ እና ከሀገሪቱ የበጎ አድራጎት ተቋማት ኮሚሽን/Charity Commission/ ባገኘው ማረጋገጫና ድጋፍ መሠረት አለመግባባቱ የተፈጠረው እና ድርድሩም መቀጠል ያለበት በአምልኮተ እግዚአብሔር ላይ ሳይሆን በሌላው ጉዳይ ላይ መሆኑን በመግለጽ ቤተ ክርስቲያኒቱም በምትከፈትበት ጊዜ ችግር እንዳይፈጠር የአካባቢውን ፖሊስ እርዳታ በመጠየቅ ታኅሣስ ፳ ቀን የሰሜን ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እንጦንስ፣ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መጋቤ አእላፍ ተወልደ ገብሩ፣ የደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ ጽዮን አባ ግርማ ከበደ፣ የደብሩ ሊቃውንት እና ካህናት፣ መዘምራን እና ምእመናን በተገኙበት በይፋ አገልግሎት መስጠቷን ቀጥላለች።

ብፁዕ አቡነ እንጦንስ ከጠዋቱ ሁለት ሰዓት ጀምሮ በቦታው በመገኘት ሥርዓተ ጸሎቱን ሲመሩ እና ቡራኬ ሲሰጡ የቆዩ ሲሆን ባስተላለፉት ቃለ ምእዳንም የሰው ጠላቱ ዲያብሎስ ብቻ መሆኑን እና ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚወዱንን ብቻ ሳይሆን የሚጠሉንንም እንድናፈቅር እንዳዘዘን በማስተማር ማንም በማንም ላይ ቂም እንዳይይዝ አባታዊ ምክር ሰጥተዋል፡፡ ለህዝቡም ጸሎተ ንስሐ ከደገሙ በኋላ ሦስት ጊዜ “ይቅር ለመድኃኔዓለም!!!” በማስባል እርስ በርስ አስታርቀዋል። በቀጣይም ተቋርጦ የነበረው አገልግሎት እንደሚቀጥል፣ ሀገረ ስብከቱ ከሰበካ ጉባኤው ጋር በመሆን አለመግባባቱን በውይይት እና በክርስቲያናዊ ፍቅር ለመፍታት እና አዲስ የሰበካ አስተዳደር ጉባኤ ለማስመረጥ እንደሚጥር ገልጸዋል።

በቤተ ክርስቲያኒቱ የተገኙ ሊቃውንት፣ ካህናት እና ምእመናን ከእንባ ጭምር በመጸለይ እና በመዘመር አምላካቸውን ያመሰገኑ ሲሆን፤ መርሐ ግብሩ በእግዚአብሔር ቸርነት ከቀኑ 7፡30 በሰላም ተጠናቋል።