addis ab 03

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የመዋቅር፣ አደረጃጀትና አሠራር ረቂቅ መመሪያ ርክክብ ተካሔደ

የካቲት 6 ቀን 2006 ዓ.ም.

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

addis ab 03ዐሥራ ሦስት የመመሪያ ረቂቅ ሰነዶችን ከ12/11/2005 ዓ.ም ጀምሮ ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሲያጠናና ሲያወያይ የነበረው 18 አባላት ያሉት አጥኚ ኮሚቴ ዛሬ የካቲት 6 ቀን 2006 ዓ.ም በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የመሰብሰቢያ አዳራሽ በተደረገው የመረካከቢያ መርሐ ግብር ረቂቅ ሰነዶችን ለብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የብፁዕ ወቅዱስ ረዳትና የጅማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አስረከቡ፡፡

በርክክቡ ወቅት ንግግር ያደረጉት የአጥኚው ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ታደሰ አሠፋ እንደገለጹት “ቡድኑ የልጅነት ድርሻውን ይወጣ ዘንድ ቤተ ክርስቲያን ሓላፊነት ስትሰጠው ወደ ዋና ጥናቱ ከመግባቱ በፊት ሥራው የተቃና ይሆን ዘንድ በአባቶች ጸሎት እንዲታሰብ መብዓ አሰባስቦ መላኩ ለጥናት ቡድኑ ብርታት እንዲሁም ሥራ መጠናቀቅ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርጐለታል፡፡ ስለዚህም የእግዚአብሔር ቸርነት የቅዱሳን ጸሎት አልተለየንም” ብለዋል፡፡

በመቀጠልም “ጥናቱን እያጠናን ከቅዱስ ሲኖዶስ እስከ አጥቢያ ምእመናን ድረስ በማወያየት 96 በመቶ ተቀባይነት ያገኘ ሲሆን በውይይቱ ወቅት እንዲካተቱ የተነሡ ነጥቦች ተካተውና ተሻሽለው ለዚህ ቀን ደርሰናል፡፡ ጥናቶቹም፡-

  1. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የመዋቅር የአደረጃጀት ጥናትና መመሪያ 119 አንቀጽ

  2. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የአብያተ ክርስቲያናት የደረጃ መስፈርት መመሪያ 23 ገጽ

  3. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የአገልግሎት መደቦች የሥራ ዝርዝር መመሪያ 120 ገጽ

  4. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሰው ኃይል ትመናና የተፈላጊ ችሎታ መስፈርት መመሪያ 53 ገጽ

  5. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የደመወዝ ስኬል ጥናት 99 ገጽ

  6. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የአገልግሎጋዮች ማስተዳደሪያ ፖሊሲና ዝርዝር የአፈጻጸም መመሪያ 125 ገጽ

  7. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሥልጠናና የሰው ሃብት ልማት ፖሊሲና ዝርዝር የአፈጻጸም መመሪያ 30 ገጽ

  8. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የፋይናንስ ፖሊሲና ዝርዝር የአፈጻጸም መመሪያ 107 አንቀጽ

  9. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የግዢ፣ ሽያጭና ንብረት አስተዳደር መመሪያ 26 ገጽ

  10. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የልማት ሥራዎች ፖሊሲና ዝርዝር የአፈጻጸም መመሪያ 16 ገጽ

  11. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የዕቅድና ሪፖርት ዝግጅት፣ ክትትልና ግምገማ መመሪያ 31 ገጽ

  12. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የኦዲትና ኢንስፔክሽን ፖሊሲና ዝርዝር የአፈጻጸም መመሪያ 57 ገጽ

  13. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሥልጠና ማእከል፣ ወላጅ አልባ ሕፃናትና የአረጋውያን መርጃ ማእከል ፕሮጀክት ጥናት ሰነድ /የተሠጠ/

ሲሆኑ የዚህ ጥናት ትግበራ ስልትና የእያንዳንዱ መመሪያና ፖሊሲ ማስፈጸሚያ ብዛት ያላቸው ቅጾች ለትግበራ ስለሚያስፈልጉ ወደፊት ተጠናቀው ይቅርባሉ”addis ab 02 በማለት ገልጸው ሰብሳቢው የአጥኚው ቡድን አባላት ለብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የጥናት ሰነዱን እንዲያስረክቡ ካደረጉ በኋላ “በዚህ ጥናቱን በሚመለከት ማብራሪያ ለሚጠይቀን አካል ሁሉ ምላሽ ለመስጠትና ለመወያየት ዝግጁ ነን” በማለት ገልጸዋል፡፡

ከአጥኚ ኮሚቴው በመቀጠል ንግግር ያደረጉት የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ አእላፍ በላይ መኰንን “እንደገለጹት ለቤተ ክርስቲያን ብላችሁ ጊዜያችሁን ገንዘባችሁን ሁሉን ነገር አውጥታችሁ የሠራችሁትን እግዚአብሔር ዋጋችሁን ይክፈላችሁ፡፡

እግዚአብሔር ለሥራ ጊዜ አለው፡፡ ሁሉም ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅም ነው፡፡ ቅዱስ አባታችንም ጥናቱ ለምን ቆየ? ከምን ደረሰ? እያሉ እየጠየቁ ነው፡፡ የተቃውሞ ጥያቄ የሚያነሱትም ነፃ አስተሳሰብ ነውና ሊመሰገኑ ይገባል” ብለዋል፡፡

ጥናቱን የተረኩበት ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ ባደረጉት ንግግር “መነሻ የሚሆን ነገር እንድናቀርብ በመጠየቃችን እናንተም ይህን በመሥራታችሁ እግዚአብሔር በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ ያድላችሁ፡፡

በእግዚአብሔር የምንጠየቀው የሚጠብቅብንን ሳንሠራ ስንቀር ነው፤ የታዘዛችሁትን አዘጋጅታችሁ አቀርባችኋል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ተግባራዊ ያደርገዋል፡፡ ሆን ብሎ ለጥፋት የሚሰለፍ የለም አስተሳሰባችን በመለያየቱ እንጂ፡፡ ከዚህ በተመሳሳይ ቃለ ዓዋዲው መጀመሪያ ሲረቀቅ ብዙ ተቃውሞ ቀርቦበት ነበር፤ ግን ተግባራዊ ሆነ፡፡ ከዚህ በኋላ የሚያስፈልገው ሁላችንም ወደ አንድ መጥተን ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅመውን ማድረግ ነው” በማለት አባታዊ ምክር ሰጠተዋል፡፡ በመጨረሻም በርክክቡ መርሐ ግብር ላይ ለተገኙት ተሳታፊዎች የደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ የምሳ ግብዣ አድርገዋል፡፡

01mkBahirDar

መንፈሳዊ ጉባኤ በባሕር ዳር ከተማ

01mkBahirDar

ጾመ ሰብአ ነነዌ

 የካቲት 3 ቀን 2006 ዓ.ም.

ርዕሰ ደብር ብርሃኑ አካል

ጾመ ነነዌ ከአዋጅ አጽዋማት አንዱ ሲሆን የምትጾመውም ለሦስት ቀናት ነው፡፡ ጾሙ የሚጀመርበት ዕለትም ልክ እንደ ዐቢይ ጾም ሰኞን አይለቅም፡፡ ጾሙ የሚጀመርበት ቀን ደግሞ ሲወርድ ወይም ወደ ኋላ ሲመጣ እስከ ጥር 17 ቀን ድረስ ነው፡፡ ሲወጣ ወይም ወደፊት ሲገፉ ደግሞ እስከ የካቲት 21 ድረስ ነው፡፡ በእነዚህ 35 ቀናት/ዕለታት/ ስትመላለስ ትኖራለች፡፡ ከተጠቀሱት ዕለታት አይወርድም አይወጣም ማለት ነው፡፡

የሦስት ቀኑን ጾም የጾሙት በነነዌ ይኖሩ የነበሩ ሕዝቦች ሲሆኑ ከተማዋ በጤግሮስ ወንዝ ዳርቻ የምትገኝ መሥራቿም ናሞሩድ ነው፡፡ ዘፍ.10፥11-12 ጥንታዊቷ የነነዌ ከተማ ለአሦር መነሻ የሆነ ከተማ እጅግ ሰፊና ያማረ ፤ የከተማው ቅጥር ርዝመት አሥራ ሁለት ኪሎ ሜትር ነበር፡፡ ሰናክሬም ብዙ ሕንፃዎችንም ሠርቶበት ነበር፡፡ /ዮናስ. 4፥11/

የነነዌ ሰዎች ኃጢአታቸው ቅድመ እግዚአብሔር ደርሶ በኃጢአታቸው ምክንያት ሊጠፉ ሲሉ ቸርነትና ምህረቱ የማያልቅበት እግዚአብሔር ነቢዩ ዮናስ መክሮ ዘክሮ እንዲመልሳቸውና ንስሐ እንዲገቡ ወደ ነነዌ ሕዝብ ሂድ አለው፡፡ ሉቃ.11፥30 ዮናስ የስሙ ትርጉም “ርግብ” ማለት ነው፡፡ በዳግማዊ ኢዮርብዓም ዘመነ መንግሥት የነበረ ነቢይ ነው፡፡ ኢዮርብዓም ሶርያውያንን አባሮ የእስራኤልን ድንበር እንዲመልስ ትንቢትን ተናግሯል፡፡ ይህ ነቢይ መኖሪያው በገሊላ በጋትሔፌር ድንበር ከተማ ነበረ፡፡ አባቱም አማቴ ይባላል ፡፡ 2ነገ14፥25፣ ት.ዮና1፥1

እግዚአብሔርም “ሄደህ በነነዌ ላይ ስበክ” ባለው ጊዜ “አልሄድም” አለ፡፡ “አንተ መሀሪ ነህ ልትጠፉ ነው ብዬ ተናግሬ ስትምራቸው ሐሰተኛ ነቢይ እባላለሁ፡፡” ብሎ ላለመታዘዝ እስራኤልን ለቆ በመርከብ ወደ ተርሴስ ሸሸ፡፡ እግዚአብሔር ግን ታላቅ ነፋስን አስነሥቶ መርከቧበማዕበል እንድትመታ አደረገ፡፡ ከዮናስ ጋር በመርከቧ ተሳፍረው የነበሩት ነጋድያንም ያላቸውን ሀብት ወደ ባህሩ መጣል ሲጀምሩ ነቢዩ ዮናስ “በእኔ ምክንያት የመጣ ስለሆነ ንብረታችሁን ሳይሆን እኔን ወደ ባህር ጣሉኝ” ብሎ ተማጸናቸው፡፡ እነሱም “የሰው ደም በእጃችን እንይሆንብን አይሆንም” አሉት፡፡ ዕጣም ቢጣጣሉ ዮናስ ላይ ወጣ፡፡ ነጋድያኑ ዮናስን ወደ ባሕሩ ጣሉት፡፡ ወዲያው የእግዚአብሔር የማዳን መልእክት ዮናስ እንዲያደርስ የታዘዘ ታላቅ ዓሣ አንበሪ ዮናስን በአፉ ተቀብሎ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት አሳድሮ ነነዌ አደረሰው፡፡ ዮናስም ከእግዚአብሔር መኮብለል አለመቻሉን ሲረዳና ነነዌ መሬት ላይ መድረሱ ሲነገረው ለነነዌ ሰዎች “ንስሐ ግቡ” ብሎ መስበክ ጀመረ ዮናስ 1እና2 ፡፡ የነነዌ ሰዎች ንስሐ በገቡ ጊዜ እግዚአብሔር ማራቸው /ዮና.3/

ነቢዩ ዮናስም ውሸታም ላለመባል መኮብለሉ ስህተት መሆኑን እግዚአብሔር ቅልን ምሳሌ በማድረግ አስረዳው፡፡ /ዮና.4/ ነቢየ ሐሰት እንዳይባልም እሳቱ እንደ ደመና ሆኖ ታይቶአል፡፡ የታላላቁ ዛፍ ቅጠል እስኪጠወልግ ድረስ አድርቆ ለሕዝቡ አሳይቷቸዋል፡፡ንስሐቸው በከንቱ እንዳልቀረ አስረድቷቸዋል፡፡ በስንክሳር ታኅሣሥ 5 እንደሚነግረን ፤ወበልዓ አሐደ ኀምለ ይላል ንስሐ ያልገቡ አንድ አገር አጥፍቶአል፡፡ ነቢዩ ኤልያስ ያስነሣው የስራጵታ መበለት ሕፃን ዮናስ እንደሆነ /1ነገሥ.17፥19/ ሲያስረዳን ፤ክርስቶስ የዮናስን ከዓሣ ሆድ መውጣት የራሱ ትንሣኤ ምሳሌ አድርጎታል፡፡ /ማቴ.12፥19-42/ ሉቃ.11፥30-32/፡፡

ጾመ ነነዌ የሦስት ቀን ሱባኤ ናት፡፡ ይሄውም አስቴር አስቀድማ ሦስት ቀን ጾማ ጸልያ በእሥራኤል ላይ የመጣውን መቅሠፍት እንዲመለስ አድርጋለች ኢሳ.4፥15-16፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ከበዓል ስትመለስ ልጇ ሕፃኑ ኢየሱስ መንገድ ላይ ጠፍቶአት ከሦስት ቀን ፍለጋ በኋላ በቤተ መቅደስ እንዳገኘችው ሁሉ ሉቃ.2፥46 ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ለሄሮድስ በሰጠው መልስ ሦስት ቀን የሱባኤ ፍጻሜ መሆኑን ገልጿል ሉቃ.13፥32፡፡

የነነዌ ሰዎች የተነሳህየን ምሳሌ ናቸው ይህም ማለት ሰው ጥፋቱን አምኖ ንስሐ ከገባ እግዚአብሔር ይቅር ማለቱን አይተውም፡፡ ለዚህም ነው ዮናስን አንተ ላልደከምክበት እና በአንድ ቀን በቅሎ ላደገ ቅል ስታዝን እነሆ በታላቂቱ ነነዌ ከተማ ያሉ ከአንድ መቶ ሃያ ሺህ በላይ ሕዝቦችና እንስሳቱ የእጄ ፍጥረቶች ስለሆኑ ያሳዝኑኛል ያለው፡፡

ዛሬ ዓለማችን በኃጢአት ማዕበል እየተናወጠች ባለበት ወቅት እኛም ብንመለስ እና ንስሐ በንገባ ቸሩ ፈጣሪያችን ይቅርታና ምሕረት የባሕርይ ገንዘቡ ስለሆነ “ወደኔ ተመለሱ እኔም ይቅር እላችኋለሁ ”ብሎ አስተምሯል፡፡ ቀደምት አባቶቻችን ይህን እና ሌሎች አጽዋማትን እንድንጾም የወሰኑልን ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ ለምሳሌ ጾመ ነነዌ የሚከተሉትን ምሳለዎች እናገኝባታለን ታሪኩን በማስታወስ የእግዚአብሔርን ቸርነትና መሀሪነት የምናስታውስበት ነው፡፡ ይኸውም ፍጥረቶቹ በበደልን ጊዜ ፈጽሞ ከማጥፋት ይልቅ ምክንያት ፈልጎ እንድንድን ያደርጋል፡፡ ዮናስ ፈቃደኛ ባይሆን እንኳ በተለየ ጥበቡ እንዲሄድ አድርጎታል፡፡ ሌላ ነቢይ አጥቶም አይደለም እሱንም ጭምር ሊያስተምረው ስለፈለገ እንጂ፡፡

በዮናስ አማካይነት የተደረጉ ተአምራትን መገንዘብና ካለመታዘዝ የሚመጣ ቅጣት ቀላል አለመሆኑን ተገንዝበን ለእግዚአብሔርም ሆነ ለሃይማኖት አባቶች አና ለወላጆች መታዘዝን እንማርበታለን፡፡ እንደ ነነዌ ሰዎች እኛም ጾመን ጸልየን ከኃጢአታችን እንድንነፃ ነው፡፡ ብንጾም እራሳችን፣ ሃገራችንን፣ እጽዋቱንና እንስሳቱም ሳይቀር በኛ በደል ምክንያት በድርቅ በቸነፈር እንዳይጠፋ እግዚአብሔር ይቅር ስለሚል ነው፡፡

ጾመን እንድናበረክት ይርዳን

ይቆየን

 

ሕይወት ተገለጠ አይተንማል

 የካቲት 3 ቀን 2006 ዓ.ም.

ዲ/ን ታደለ ፈንታው

ስለሕይወት ቃል ከመጀመሪያ የነበረውንና የሰማነውን በዓይኖቻችንም ያየነውን የተመለከትነውም እጆቻችንም የዳሰሱትን እናወራለን፡፡ ሕይወትም ተገለጠ አይተንማል፡፡እንመሰክራለንም፡፡/1ኛ ዮሐ 1፡1/

ቅዱስ ዮሐንስ በቀዳማይ መልእክቱ ለዓለም የሚያስተዋውቀው ሕይወት ዓለም የማያውቀው አስቀድሞ ከእግዚአብሔር አብ ዘንድ የነበረ በኋለኛው ዘመን ሰው ይሆን ዘንድ ሥጋን ተዋሕዶ በምድር ላይ ይመላለስ ዘንድ የወደደ፣ ከአብ ዘንድ የነበረውን፣ ለእኛም የተገለጠውን ሕይወት ነው፡፡ አስቀድሞ በወንጌሉ ይህንን ሕይወት ‹‹ በመጀመሪያ ቃል ነበረ፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ፤ ሁሉ በእርሱ ሆነ ከሆነው አንዳች ስንኳ ያለእርሱ አልሆነም/ዮሐ 1፡1/ በማለት የገለጠው ነው፡፡

ወንጌላዊው ከመጀመሪያ የነበረውን ሲል እያስተማረን ያለው ቀዳማዊ ቃል ዘመን የማይቆጠርለት መሆኑንና በየዘመናቱ የሰራው ታላቅ ሥራ መገለጡን የሚያመለክት ነው፡፡ እርሱ ከባህርይ አባቱ ከእግዚአብሔር አብ ጋር ህልው ሆኖ የሚኖር ነው፡፡ አይቀዳደሙም፣ ወደኋላ አይሆኑም፡፡ አብን መስሎ አብን አክሎ የተወለደ ነው፡፡ በኅላዌ ፣በአገዛዝ፣ በመለኮት፣ በአገዛዝ፣ በመለኮት፣ ከባሕርይ አባቱ ጋር የተካከለ ነው፡፡

እርሱ ዘላለማዊ ቃል ነው የሚለው በመጀመሪያ ቃል ነበረ በማለት በወንጌሉአስቀድሞ ገልጦታል፡፡ነገር ገን ዓይኖቻችን የተመለከቱት የሚለው ቃል የሚያመለክተው የጌታን መገለጥ ነው፡፡ እጆቻችን የዳሰሱትንም የሚለው ቃል ተመሳሳይ እሳቤን ይይዛል፡፡ አካላዊ ቃል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተገልጦ ስጋን ተዋሕዶ ባይታይ ኑሮ የሰው ልጆች ባልተመለከቱት አብረውት ባልበሉ ባልጠጡም ነበር፡፡ ስለጌታ የሚኖረን እውቀት፣ ስለሃይማኖታችን የሚኖረንም መረዳት በማየት ላይ የሚቆም አይደለም፡፡ የሚመሰከርም ነው እንጂ፡፡ ምስክርነት የሚለው ቃል ሰማእትነትን የሚያመለክት ነው፡፡ አይተንማል ስለዚህ በስምህ ልንሰደድ ፣ልንገረፍ፣ ወደ ወኅኒ ልንጋዝ፣ ልንሰደድ አስፈላጊም ሆኖ ሲገኝ ልንሞት ተዘጋጅተናል ማለት ነው፡፡ ሰማእታት በእውነት ምስክርነታቸው የተቀበሉት መከራ ብዙ ነው፡፡ ምስክርነታቸውም ለሰሙትና ላዩት ቃል ነው፡፡ ምስክርነት በቃል ፣ በኑሮ/በሕይወት/ በሥራ፣ የሚገለጥ ነው፡፡ የክርስቲያኖች ምስክርነት የሚሰሙአቸውን ወጎኖች ያስቆጣቸዋል፤ ይህንን ሁኔታ ተከትሎ የእውነት ምስክር የሚሆን ክርስቲያን ፍጻሜ ሰማእትነት ነው፡፤ ሰዎች ስለእረሱ ይመሰክሩ ዘንድ እግዚአብሄር ፈቃደ ነው፡፡ ስለዚህም ነው መድኃኒታችን ‹‹ በሰው ፊት የሚመሰክርልኝን በሰማይ አባቴና በመላእክቱ ፊት እመሰክርለታለሁ በሰው ሁሉ ፊት የሚክደኝን በሰማይ አባቴና በመላእክቱ ፊት እክደዋለሁ በማለት የተናገረው፡፡››

ከጌታ መገለጥ አስቀድሞ ሰው ልጅ ይኖር የነበረው ከእግዚአብሔር ቁጣ በታች ሆኖ በመርገም ነበር፡፡ እግዚአብሔርን ተግተው ይፈልጉ ያገለግሉ የነበሩ ነቢያት ይህንን ሁኔታ ‹‹ጽድቃችን እንደመርገም ጨርቅ ነው/ኢሳ 64፡6/ በማለት የተናገሩለት ነው፡፡ ይሁን እንጂ እግዚአብሔር አሕዛብን እርሱን ተመራምረው የሚረዱበትን መንገድ ሳያመለክት እንዲሁ አልተዋቸውም ነበር፡፡ ነገር ግን በዚህየፈጣሪን ሀልወቆት በሚገልተው መንገድ ተጉዘው ወደ እውነተኛው አምላክ መድረስ ሳይቻላቸው ቀርቷል፡፡ እግዚአብሄር ሀልዎቱ የተገለጠበትን ድንቅ ሥራውን የሚመሰክርበትን ዓለም በኃጢአት አቆሸሹት፡፡ ራሳቸውንም በደለኛ አደረጉ፡፡ የእግዚአብሔርም ቁጣ የሚገባቸው ሆኑ፡፡ የአሕዛብም ጣዖት ማምለክ እግዚአብሄርን አስቆጣው፡፡ ምክንያቱም ከፈጣቲ ይልቅ ፍጡርን ፍጡርንም የሚያስተውን አጋንንትን ለማምለክ ፈቅደዋልና፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን ጥቁር የኃጢአት መልክ እንደሚከተለው ይገልጠዋል፡- ‹‹እግዚአብሔር ስለገለጠላቸው ስለ እግዚአብሄር ሊታወቅ የሚቻለው በእነርሱ ዘንድ ግልጥ ነውና፡፡ የማይታየው ባህርይ እርሱም የዘላለም ኃይሉ ደግሞም አምላክነቱ ከዓለም ፍጥረት ጀምሮ ከተሠሩት ታውቆ ግልጥ ሆኖ ይታያልና፤ ስለዚህም እግዚአብሔርነቱን እያወቁ እንደ እግዚአብሔርነቱ ባላከበሩት መጠን ስላላመሰገኑትም የሚያመካኙት አጡ፤ ነገር ግን በአሳባቸው ከንቱዎች ሆኑ፤ የማያሥተውለውም ልባቸው ጨለመ፡፡ ጥበበቦች ነን ሲሉ ደንቆሮዎች ሆኑ፤የማይጠፋውንም የእግዚአብሔር ክብር በሚጠፋ ሰውና በወፎች አራት እግር ባላቸው በሚንቀሳቀሱትም መልክ ለወጡ፡፡/ሮሜ 1፡18-27/

አይሁድ የነበሩበት ሁኔታ ከአሕዛብ እምብዛም የተሻለ አልነበረም፡፡ አይሁድ ከአሕዛብ የሚለዩበት ምቹ ሁኔታዎች ነበሩአቸው፡፡ በብሉይ ዘምን በተለያየ ጌዜ የተደረገው መገለጥ፣ ሕጉ፣ ነቢያት ቀዱሳት መጻሕፍት ነበሩአቸው፡፡ እነዚህ ሁሉ ነገሮች በደላቸውን ከማብዛት ውጪ አንዳች የጠቀሙአቸው ነገር አልነበረም፡፡ አሕዛብ ጣዖት በማምለክ ወጥመድ ሲያዙ ሕጉ ግን ሊመጣ ስላው ክርስቶስ ይናገር እንደነበረ አላስተዋሉም፡፡ አሕዛብ ጣዖት በማምለክ ወጥመድ ሲያዙ አይሁድ የሕጉን ነጠላ ትርጓሜ ፊደልን በማምለክ ተያዙ፡፡ ሕጉ ግን ይመጣ ስላለው ክርስቶስ ይናገር እንደነበረ አላስተዋሉም እንደመሰላቸው ተረጎሙት እንጂ፡፡ በብሉይ ኪዳን የነበሩ ቅዱሳን ሕጉን ባለና በሌለ ጉልበታቸው በመፈጸም ወደ ቅድስናና ፍጹምነት ለመድረስ ይጣጣሩ ነበር፡፡ ይህ ሰውኛ ጥረት በሕግም እንዲገኝ ይፈለግ የነበረው ጽድቅ ሰዎች ስለራሳቸው የነበረቸው አመለካከት እንዲዛባ፣ ራሳቸውን ከፍ አድርገው እንዲመለከቱ‹‹ ጌታ ሆይ እኔን እንደቀራጩ ስላላደረግኸኝ አመሰግንሃለሁ›› እንዲሉ አድርጓቸዋል፡፡

በአንጻሩ በሕጉ ጥላ ሥር የነበሩ ጉድለታቸውን የተገነዘቡ ወገኖች መራራ የሆነ የኃዘን ስሜት ተሰምቶአቸው ‹‹ እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ፣ ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል? በማለት ጩኸታቸውን አሰምተዋል፡፡ /ሮሜ 7፡24/ አሁን እየጠናገርነው ላለው ነገር ማሳያ ምሁረ ኦረት ከነበረው ለአባቶቹ ወግና ሥርዓት ይጠነቀቅ ከነበረው የቀድሞው ሳውል የኋለኛው ብርሃና ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ የበለጠ ምስክር ሊሆን የሚቻለው ወገን የለም፡፡ ኢክርስቲያናዊ ከሆነው ወግና ልማድ ወጥቶ ክርስቲያናዊ በሆነው መስመር ለመጓዝ ቅዱስ ጳውሎስ የራሱን የሕይወት ተሞክሮ ይነግረናል፡፡ በቅዱስ ጳውሎስ የተደረገ ለውጥ ሥሩን ዘልቆ መሰረቱን ነክቶ የተደረገ ክርስቲያናዊ ለውጥ ነበር፡፡ ካለፈው ወጉና ልማዱ ፈጽሞ የሌው ነው አዲስ የሆነ የሕይወት ፍልስፍና የኑሮ መስመርም እንዲከተል ያደረገው ነው፡፡ ሕይወትና ሞት በማነጻጸር ሊገለጥ የሚችል ለውጥ ነው፡፡ ወደ ክርስቶስ ሞት ይገባ ዘንድ ሞቱንም በሚመስል ሞት ይተባበር ዘንድ እንዳደረገ ክርስቲያኖችም አስቀድመው ከሚገዙለት ዓለም ወጥተው ለዓለም ሊሞቱ ይገባቸዋል፡፡ ሞቱን በሚመስል ሞት ይተባበሩ ዘንድ ይህ ነገር አስፈላጊ ነው፡፡ ከክርስቶስ ገር መሞትም መቀበርም መነሳትም የሚቻለው በዚህ መንገድ ነው፡፡/ሮሜ 6፡2-8፣ ገላ 2፡20፣ቆላ 3፡3/ ከክርስቶስ ጋር የሚነሳው አዲሱ ሰው የሚወለደው በዚህ መንገድ ነው፡፡ እርሱም ክርስቲያን የሚለውን ስም የተሸከመና ከሥምም በላይ የሆነውን ስም ገንዘብ የሚያደርግ ነው ፡፡ የጌታ መገለጥ ዓላማው ይህ ሁኔታ ይፈጸም ዘንደ ነው፡፡

በክርስቶስ መገለጥ አዲስ ስምን ገንዘብ ያደረገው መንፈሳዊው ሰው የራሱ የሆነ ግላዊና ዓለማዊ ጠባያትን አስወግዶ ባህርይውን ከክርስቶስ ባህርይ ጋር ማስማማት የሚያስችለውን የመንፈስ ማሰሪያ ገንዘብ ለማድረግ የሚታገል መላ ዘመኑን በፍርሃትና በመንቀጥቀጥ የሚመላለስ የእግዚአብሔርንም እውነጠኛ ፍቅሩ በልቡናውቋጥሮ የሚመላለስ ነው፡፡

 

ክርስቲያናዊ ሕይወት ከክርስቶስ ጋር መቀበር ነውና ከዓለምና ከኃጢአት መለየትን ይጠይቃል፡፡/ኤፌ 2፡13/ ይህ ከዓለምና ከኃጢአት መለየት በክርስቶስ የመስቀል ላይ የማዳን ሥራ የተገለጠ ነው፡፡ ‹‹አይዞአችሁ እኔ ዓለሙን አሸንፌዋለሁ››በሚለው እውነተኛ የአዋጅ ቃልም የታጀበ ነው፡፡ አማናዊ የሆነ የአዋጅ ቃልም ነው፡፡ በነፍሳችን መልሕቅ ልዩ ሥፍራ ያለው ነው፡፡ ክርስቲያኖች ክርስቶስን ይለብሱታል፡፡ በመድረክ ላይ የሚጫወት ተዋናይ መድረኩን እንዲያደምቅለት በመድረክ ላይ ሳለ የሚለብሰው ከመድረክ ሲለይ የሚያውቀው የትወና ልብስ ዓይነት አይደለም፡፡ በመሰዊያው ፊት ለፊት ክርስቶስን ወክሎ የክርስቶስ ወኪል እንደሆነው ካህን ነው እንጂ፡፡ ካህኑ ክርስቶስን ወክሎ እንደሚናገር ክርስቶስን የለበሰ ክርስቲያንም በእርሱ የክርስቶስ ሕይወት ይታያል፡፡ በመውጣቱ፣ በመግባቱ፣ በኑሮው፣ በድካሙ የሚታየው መልክ ሕያው የሆነ የክርስቶስ መልክ እንጂ አስቀያሚ የሀኖነ ዓለማዊ ሰው መልክ አይደለም፡፡

በዚህ ሁኔታ ክርስቲያናዊ ሕይወትን ስንመለከተው ተራ የሆነው የዕለት ዕለት የዚህ ዓለም ኑረሮአችን አላፊ ጠፊ የማይጠቀም ሆኖ እንመለከተዋለን፡፡ በዚህ ዓለም የምናደርገው ስጋዊ ሩጫም አንድ ቀን በሞት ፍጻሜውን እንደሚያገኝ እንረዳለን፡፡ ቅዱሳን የዚህ ዓለም ኑሮ ቀናት እየገፉ በሄዱ ቁጥር የማይጠቅም እንደነበረ ተገንዝበዋል፡፡ ይህንም ሁኔታ ለማሰወገድ ጠንካራ ጦርነት ላይ ነበሩ ከዓይን አምሮትን ከሥጋ ፍላጎት ጋር ተዋግተዋል፡፡ ታግለውም አሸንፈዋል፡፡ ይህን ዓለም ተዋግተው ወደ ውጭ በገፉት መጠን በልብ ውስጥ ወዳለው ወደ ተሰወረው የልብ ሰው ይመለከቱ ዘንድ እግዚአብሔር ረድቶአቸዋል፡፡ የቅዱሳን ሕይወትና ሥነ ምግባር የተቀረጸው በልባቸው ላይ በነገሰው በክርስቶስ አማካኝነት ነው፡፡

ከቅዱሳን አንዱ እንዲህ ይላል፡- እግዚአብሄርን በሕይዎታችን ሲሰራ እንመልከተው፡፡ ለሥራው መልስ በመስጠት ምስክር እንሁን፡፡ ክርስቲያናዊ ሃይማኖትንና ምግባርን ይዘን እንገኝ፡፡ የክርስቶስን መልክ ለብሰን ስለእርሱም ዕለት ዕለት የምንሞት ብንሆን በነፍሳችን ተጠቃሚዎች ነን፡፡ በማየትና በማመን መካከል የገዘፈ ልዩነት አለ፡፡ በተግባር የምንኖረው ሕይወት ሰዎች ካልኖሩበት ትርጉሙን ላይረዱት ይችላሉ፡፡ ብዙ ምስጢራትን የምንገነዘባቸው በእምነት ሕይወት በማደግ እንጂበቃላት የመይገለጡ፣ ከቃላትም የመግለጥ አቅም በላይ የሆኑ ጉዳዮች አሉ፡፡ ቃላት የማያውቁትን ነገር ማስረዳት አይቻላቸውምና፡፡ ወደ እርሱ መቅረብ ማንም ወገን የማይቻለው እውነተኛ ብርሃን ዘመዶቹ ሊያደርገን በወደደ ጊዜ በሥጋ ተገለጠ፡፡ ይህም መልካም በመሆኑ ምክንያት እንጂ በጽድቅ ሥራችን የተነሣ አይደለም፡፡ ይህን ሁኔታ አውቀን ከፊታችን ያለውን ሩጫ በእምነት መሮጥ ይቻለን ዘንድ አምላካችን ይርዳን፡፡

 

የሰናፍጭ ቅንጣትማቴ 13÷31

 ጥር 30 ቀን 2006 ዓ.ም.

 

ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መላክ
በምዕ/ጎጃም ሀገረ ስብከት
የ፬ቱ ጉባኤያት መምህር

 

 

ታላቅነትን በታናሽነት ሰውራ የያዘች እንከን የለሽ፤ዙሪያዋን ቢመለከቷት ነቅ የማይገኝባት አስደናቂ ፍጥረት ናት፡፡ የሰናፍጭ ቅንጣት፡፡ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስወንጌልን በምሳሌ ካስተማረባቸው መንገዶች አንዱ ሰናፍጭ ነው፡፡ ስትዘራ ታናሽነቷ ስትበቅል ግን ታላቅነቷ የገዘፈ ምሥጢር ያለው በመሆኑ ለዚህ ተመርጣለች በመጽሐፍ እንደተባለ ሰናፍጭ ስትዘራ እጅግ ታናሽናት ስትበቅል ግን ባለብዙ ቅርንጫፍ እስከመሆን ደርሳ ታላቅ ትሆናለች ከታላቅነቷ የተነሳ እጅግ ብዙ አእዋፍ መጥተው መጠጊያ እንደሚያደርጓትም አብሮ ተገልጿል አሁን ታናሽነቷን በታላቅነት መሰወር ችላለችና ብዙዎችን ልታስገርም ትችላለች፡፡

ይህ ምሳሌ ታላቅነትን በታናሽነት ሰውራ ይዛ የኖረችውን የክርስቶስ ቤተ ክርሰቲያን ነው እንጅ ሌላ ምንን ያመለክታል? የሰናፍጭ ቅንጣት ብሎ የጠራት አካሉ የሆነችውን ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ ምክንያቱም እንደ ሰናፍጭ ሁሉ ሲዘራት ትንሽ ነበረች፡፡ በመቶ ሃያ ቤተሰብ ብቻ የተዘራች ዘር ናት፡፡የእግዚአብሔርን ምሥጢር ልብ አድርጉ ኦሪትን ሲመሰርት እንዲህ ነበርን? በሙሴ ምክንያት በስድስት መቶ ሺህ ህዝብ መካከል የሰራት አይደለምን? ወንጌልን ግን እንዲህ አይደለም ከመቶ ሃያ በማይበልጡ ሰዎች መካከል ሰራት እንጅ ፡፡ወደሕይወት የሚወስደው መንገድ የጥቂቶች ብቻ መሆኑን ሲያሳየን ይህን አደረገ፡፡

ሰናፍጭ ካደገች በኋላ ለብዙዎች መጠጊያ እስኪሆን ድረስ ብዙ ቅርንጫፍ እንድታወጣ ቤተ ክርስቲያንም የዓለም መጠጊያ የሰው ልጆች መጠለያ ናት፡፡ ኦሪት በብዙዎች መካከል የተሰበከች ብትሆንም ቅሉ ቅርንጫፏ ከቤተ እስራኤል ወጥቶ ለሞዓብና ለአሞን ስንኳን መጠጊያ ሊሆን አልቻለም፡፡ ቤተክርስቲያን ግን ቅርንጫፏ ከምድር እስከ ሰማይ ደርሶ ሰማያውያኑንና መሬታውያኑን ባንድ ማስጠለል ይችላል ሙታን ሳይቀር መጠለያቸው ቤተክርስቲያን ናት እንጅ ሌላ ምን አላቸው፡፡ከዚህም የተነሳ‹‹ ሰናይ ለብዕሲ መቅበርቱ ውስተ ርስቱ፤ለሰው በርስቱ ቦታ መቀበሩ መልካም ነው ››እያሉ ሥጋቸውን በቤተክርስቲያን ነፍሳቸውን በገነት እንዲያኖርላቸው ይማጸናሉ፡፡

ቤተ ክርስቲያን እንደ ሰናፍጭ ካልቀመሷት በቀር ጣዕሟ የማይታወቅ ታናሽ የምትመስል የሰናፍጭ ቅንጣት ናት ለቀመሷት ሁሉ ደግሞ ጣዕሟ በአፍ ሳይሆን በልብ የሚመላለስ ከደዌ የሚፈውስ ነውና ቀርባችሁ ጣዕመ ስብከቷን ፣ጣዕመ ዜማዋን ፤ጣዕመ ቅዳሴዋን እንድትቀምሱ አደራ እላችኋለሁ፡፡ከዚሁሉ ጋራ ርስታችሁ ናትና ከአባቶቻችሁ በጥንቃቄ እንደ ተረከባችሁ ለቀጣዩ ትውልድ እስክታስረክቡ ድረስ የተጋችሁ እንድትሆኑና የጀመራችሁን መንፈሳዊ ተጋድሎ በትጋት እንድትፈጽሙ መንፈስ ቅዱስን ዳኛ አድርጌ አሳስባችኋለሁ፡፡

ኃያሉ አምላክ ልዑለ ባሕርይ እግዚአብሔር በቸርነቱ የሀገራችን ኢትዮጵያን አንድነት የኦርቶዶክስ ተዋህዶቤተ ክርስቲያናችንን ዕድገት ለዘለዓለሙ ይባርክ፡፡

 

የአብነት መምህራን የምክክር ጉባኤ ሊካሄድ ነው፡፡

 

ጥር 29 ቀን 2006 ዓ.ም.

በታመነ ተ/ዮሐንስ

የማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የአብነት መምህራን የምክክር ጉባኤን ለሦስተኛ ጊዜ በሀገር አቀፍ ደረጃ ሊያካሂድ ነው፡፡ መርሐ ግብሩ ከየካቲት 6 እስከ 9 ቀን 2006 ዓ.ም ለሦስት ተከታታይ ቀናት ይከናወናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በመርሐ ግብሩ ይዳሰሳሉ ተብለው ከተያዙ አጀንዳዎች መካከል የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ነጻ የትምህርትና ሥልጠና ዕድል፣ የአብነት ት/ቤቶች የጤና ግንዛቤን ባካተተ እና ትርጓሜ መጻሕፍትን በተመለከተ በዋነኝነት የሚነሡ ርዕሰ ጉዳዮች ሲሆኑ፤ የአብነት ት/ቤቶች የምስክር አሰጣጥና የአገልግሎት ሁኔታ እና ሌሎች ተዛማጅ ርዕሰ ጉዳዮችም ይወሳሉ፡፡

ይህ ጉባኤ ከዚህ ቀደም ከተካሄዱት መርሐ ግብራት ለየት የሚያደርገውን የዋና ክፍሉ ዳይሬክተር ዲ/ን አእምሮ ሲገልጹ “የአሁኑ የምክክር ጉባኤ ለየት ባለመልኩ የሚያጠነጥነው ከሀገሪቷ የትምህርትና የጤና ፖሊሲ ጋር ተደጋጋፊነት ባለው መልኩ ሲሆን፤ ይህም በሀገር ልማት ላይ ያለንን ተሳትፎ የሚጨምር ነው፡፡” ብለዋል፡፡ አያይዘውም በዚህ በተያዘው ዕቅድ መሠረት መጓዝ ከተቻለ የአብነት ተማሪዎችን መደበኛ ትምህርት የመደገፍ ትልም ተጠናክሮ በመቀጠል የአንድ ለአንድ የትምህርት አሰጣጥን ከአንደኛ ደረጃ እስከ ሁለተኛ ደረጃ እስኪደርሱ ተግባራዊ ለማድረግ ያስችላል፤ በዚህም የአብነት ተማሪዎቹ በሁለት ወገን የተሳለ ሰይፍ እንዲሆኑ እንደሚያግዛቸው አውስተዋል፡፡ በዚህም መሠረት የነገ የቤተ ክርስቲያን ተረካቢ የሆኑትን የአብነት ተማሪዎች መደገፍ አስፈላጊ መሆኑን አክለዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ከተለያዩ አኅጉረ ስብከቶች የተውጣጡ ከ200 በላይ የአብነት መምህራን የሚገኙ ሲሆን ለሦስት ተከታታይ ቀናት በግዮን ሆቴል፣ በቅርስ ጥበቃ ባለሥልጣንና በስብሰባ ማእከል(6ኪሎ) ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት ይካሂዷል፡፡ በዚህም መሠረት በስብሰባ ማእከል(6ኪሎ) የካቲት 9 ቀን 2006 ዓ.ም ከቀኑ ከ7፡30 ጀምሮ በሚከናወነው የመዝጊያ መርሐ ግብር ላይ ምእመናን በመታደም የበረከቱ ተሳታፊ ይሆኑ ዘንድ ሓላፊው ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

ሐዋርያዊ ጉዞ በምሥራቅ ኢትዮጵያ

 

 ጥር 29 ቀን 2006 ዓ.ም.

በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ክፍል አስተባባሪነት ከጥር ፲፮ እስከ ፳፭ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም ለአሥር ተከታታይ ቀናት በምሥራቅ ኢትዮጵያ ሲካሔድ የሰነበተው ሐዋርያዊ ጉዞ ተጠናቀቀ፡፡

በሐዋርያዊ ጉዞው ከጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ክፍል አባላትን ጨምሮ የማኅበረ ቅዱሳን መምህራን፣ መዘምራንና ጋዜጠኛ በድምሩ ሃያ አራት አባላት ያሉት የልዑካን ቡድኑ መነሻውን ከዋናው ማእከል ማኅበረ ቅዱሳን በማድረግ በአፋር፣ ድሬዳዋ፣ ምሥራቅ ሐረርጌና ሱማሌ ሀገረ ስብከት በመዘዋወር ሰፊ የስብከትና መዝሙር አገልግሎት ፈጽሞ ጥር ፳፮ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም ሲመለስ የማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከል አባላት ደማቅ አቀባበል አድርገውለታል፡፡

የልዑካን ቡድኑ ጥር ፲፮ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም በአፋር ሀገረ ስብከት አዋሽ ከተማ ሲደርስ የአፋር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዮናስ ጉባኤውን በጸሎትና ቡራኬ ከፍተው ጉባኤው ለሦስት ተከታታይ ቀናት በአዋሽ መንበረ ፀሐይ ቅድስት ሥላሴና ደብረ ሲና ቅድስት ማርያም ተካሒዷል፡፡

በመቀጠልም ጥር ፲፱ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም ወደ ድሬዳዋ ሀገረ ስብከት በማምራት በድሬዳዋ ኆኅተ ሰማይ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ለሁለት ቀን አገልግሎት ተሰጥቷል፡፡ በምሥራቅ ሐረርጌ ደብረ አሚን ተክለ ሃይማኖትና ጅግጅጋ ደብረ መዊዕ ቅዱስ ሚካኤል አብያተ ክርስቲያናት ሁለት ሁለት ቀን የፈጀ ተመሳሳይ አገልግሎት ተፈጸሟል፡፡

የልዑካን ቡድኑ ከተያዘለት ዕቅድ በተጨማሪ በአፋር ሀገረ ስብከት መልካ ወረር ደብረ መድኀኒት መድኀኔዓለም፣ በድሬዳዋ ሳባ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል፣ በድሬዳዋ ደብረ መንክራት ቅዱስ ዑራኤል፣ በጅግጅጋ ምሥራቀ ፀሐይ ኪዳነ ምሕረት አብያተ ክርስቲያናት ጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የስብከተ ወንጌል አገልግሎት እንደነበር የልዑካኑ አስተባባሪ መጋቤ ሃይማኖት ለይኩን ገልጸውልናል፡፡

በእያንዳንዱ ሀገረ ስብከት ጉባኤ ሲካሔድ ምእመኑ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይል የፀሐዩን ግለትና የሌሊቱን ውርጭ ተቋቁሞ እስከ ምሽቱ 3፡30 ድረስ ጉባኤውን ታድሟል፡፡

 

ገነትህን ጠብቅ ዘፍ.2፡15

 

ጥር 26 ቀን 2006 ዓ.ም. 

ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መላክ
በምዕ/ጎጃም ሀገረ ስብከት
የ፬ቱ ጉባኤያት መምህር

እግዚአብሔር አምላክ ሰውን ካሰለጠነባቸው ስፍራዎች መካከል አንዱ ኤዶም ገነት ነች፡፡ ታላቁ መጽሐፍ እንደሚነግረን “እግዚአብሔር አምላክም በስተምስራቅ ኤዶም ገነትን ተከለ የፈጠረውንም ሰው በዚያ አስቀመጠው” ካለ በኋላ ገነትን እንዲጠብቃትና እንዲንከባከባት ሓላፊነትን ሰጥቶታል፡፡

ገነት የአራቱ አፍላጋት መነሻ ሰው ከፍሬው ተመግቦ ለዘለዓለም ሕያው የሚሆንበት የዕፀ ሕይወት መገኛ ነበረች፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ሐዋርያው አትናቴዎስ በቅዳሴው ስለገነት ውበት ሲገልፅ ዕፅዋቶቻቸው ቅጠላቸው እስከ 15 ክንድ ይደርሳል፡፡ መዓዛቸው ልብን ይመስጣል፡፡ ፍሬአቸው ከጣዕሙ የተነሣ ሁሌም ከአፍ አልጠፋም ብሎ ነበር፡፡

በዚህ ሁኔታ ልዩ ምድራዊ ገጽታ ተሰጥቷት የተፈጠረችውን ቦታ እንዲኖርባት የተፈቀደለት ሰው ብቻ ነበር፡፡ እንዲኖርባትም ብቻ ሳይሆን እንዲጠብቃትም እንዲንከባከባትም rደራ የተባለው እርሱ ነው፡፡ የተበጀችውን ገነት ምኗን ያበጃታል? እንዲያው በሥራው ሁሉ ሲያሰለጥነው ነው እንጂ፡፡ ለጊዜው ያችን ከምድር ሁሉ የሚመስላት የሌለ ገነት የተባለችውን ቦታ እንዲጠብቃት ነበር ትዕዛዝ የተላለፈለት ገነት ሦስት ዓይነት ትርጉም አላት፡፡

 

1ኛ ሕይወተ አዳም፡- የመጀመሪያው የገነት ትርጉም ህይወተ አዳም ነው፡፡ ገነት በአማሩና በተዋቡ እፅዋት የተሞላች ጣፋጭ መዓዛ ፣ ፍሬ የማይታጣባት ቦታ ነበረች ህይወተ አዳምም ስትሰራ ልምላሜ ነፍስ ፤ መዓዛ መንፈስ ቅዱስ ፍሬ ክብር የተሞላች እንደነበረች ያሳያል፡፡ ሰይጣን እስኪያጠወልጋት ድረስ የአዳም ህይወት ልምላሜ ይታይባት ነበር፡፡ እግዚአብሔርም ገነትን ጠብቃት ሲለው ህይወትህን ጠብቃት ሲለው ነው፡፡ ከሁሉም በላይ አዋቂ ነውና በህይወቱ ላይ ስልጣን የተሰጠውም ፍጡር ነበር፡፡ መጠበቅም ብቻ ሳይሆን መንከባከብም ለእርሱ የተሰጠ ሓላፊነት ነበር፡፡ ዐቂበ ህግ (የታዘዘውን ህግ መጠበቅ) የህይወቱ መጠበቂያ መንገድ ሲሆን ለእግዚአብሔር የሚያደርገው አገልግሎት ደግሞ ገነት ለተባለች ህይወቱም መንከባከቢያ መንገድ ነው፡፡
በስተምስራቅ በኩል የተተከለች ምስራቃዊት ቦታ በመሆኗ ደግሞ ሌላው አስደናቂ ምስጢር ነው፡፡ ምስራቅ የብርሃን መውጫ ነው፡፡ ከምስራቅ የወጣው ብርሃን ለአራቱ መዓዘናት ሁሉ ይበቃል፡፡ ሰውም ከርሱ በሚወጣው ጥበብ ዓለምን ለውጦ የሚኖር ልዩ ፍጡር መሆኑን ያመለክታል፡፡

ወንድሜ ሆይ ገነትህን እንዴት እየጠበካት ነው አሁንም ከነሙሉ ክብሯ ነው ያለችው፤ እርግጠኛ ነህ ዛሬም እንደጥንቱ ሁሉ ለማየት ደስ የሚያሰኘውን ለመብላትም መልካም የሆነውን ዛፍ በአንተ ገነት ውስጥ ማግኘት ይቻላል፤ እውነት እልሃለው ያንተን ገነት ለመጎብኘትና ከገነትህም ፍሬ ለመብላ ገነትህን የፈጠረ ጌታ ወደ አንተ እንደሚመጣ ታላቁ መጽሐፍ ይናገራል፡፡

 

‹‹ወልድ አሁየ ወረደ ውዕቱ ገነቱ ወይብላዕ እምፍሬ አቅማሂሁ›› ወደ ገነት ገባ መልካሙንም ፍፌ ይበላ ዘንድ መኃ 4፡16 መልካም ፍሬ ለማስገኘት ምን ያህል ትተጋለህ፤ አንተ ወዳለህበት ገነት ሲመሽ የህይወትህ መዝጊያ ሰርክ ላይ ድምፁን እያሰማ ፈጣሪህ መምጣቱን እንዳትዘነጋ፡፡ ለነገሩማኮ! ያንተገነት መስሎ የተሰራ ሁሉ የተሟላለት ቦታ ማግኘት አይቻልም፡፡ አንተኮ የታዘዝከው እንድትጠብቅና እንድትንከባከብ እንጅ ምንም እንድትጨምር አይደለም፡፡ ምንም እንኳ አንዳንድ ጊዜ ገነትህን ሊያጠወልጉ የሚችሉ ነገሮች ቢኖሩም እግዚአብሔር ግን ያንተን ገነት እንዲሁ አልተዋትም፡፡ መልሰው ወደልምላሜዋና ወደቀድሞ ውበቷ ይመልሷት ዘንድ በውስጧ የሚመላለሱ አራት አፍላጋትን በነዚህ አፍላጋት ህይወት ሰጭነት ገነትህን በህይወት ማኖር ትችላለህ፡፡ አራቱ አፍላጋት የሚባሉት አራቱ ወንጌላውያን ናቸው፡፡ ያንተን ገነት ከልምላሜ አዕምሮ ወደፅጌ ትሩፋት ከፅጌ ቱርፋት ወደፍሬ ክብር እንዲያደርሱ የተፈጠሩ ናቸው፡፡ በገነት ውስጥ በገነትህ ውስጥ እንዲፈሱ አድርጋቸው፡፡ በገነትህ ውስጥ የበቀለው እፀ ህይወትም የተሰጠህን ልጅነት ያመለክታል፡፡ ያንተ ገነት ማለት በነዚህ ሁሉ ስጦታዎች የተሞላች በመሆኗ የጠላት ዓይኖች በደጅ ስለሚያደቡባት ልትጠነቀቅላት ይገባል፡፡ በሀይማኖት ጠብቃት በጾም በጸሎት በስግደት ተንከባከባት፡፡ በገነትህ መካከል የፈጣሪው ድምፅ ሲሰማ የሚሸሸግ እርቃኑን የቆመ አዳም የተሸሸገባት እንዳትሆን ገነትህን ልትመለከታት ይገባሃል፡፡ ገነትህነን ጠብቃት ተንከባከት

 

፪ኛ የገነት ትርጉም ዓለመ ቅዱሳን ገነተ ፃድቃን ክርስቶስ ነው፡፡ ፃድቃን በዚች ምድር ሲሆኑ አረጋዊ መንፈሳዊ እንደተናገረው ክርስቶስን ዓለም አድርገው ይኖራሉ፡፡ ከዕለታት በአንድ ቀን የአረጋዊ መንፈሳዊ ወንድሙ ዮሐንስ በበርሃ የሚኖር ወንድሙ አረጋዊን ራስህን የምታስጠጋበት ጎጆ ልስራልህን፤ ብሎ ላቀረበለት ጥያቄ ሲመልስ ‹‹ የሁሉ ማረፊያ ጌታ ;; ለኔ ማረፊያነት አነሰኝን ብሎ ነበር የመለሰለት ስለዚህ ፃድቅ በአፀደ ስጋ በአፀደ ነፍስ ማረፊያ ገነታቸው ክርስቶስ ነው፡፡ ለዚህም ነው በመጀመሪያ ጊዜ በምድር ላይ ፅድቁ ለተረጋገጠለት ለፈያታዊ ዘየማን ዛሬ በገነት ትኖራለህ ሉቃ 23፡43 የሚል መልስ የተሰጠው ጥበበኛ ሰው ሰለሞንም የክርስቶስን ወደዚህ ዓለም አመጣጥ ሲገልፅ ‹‹ ውዴ በገነቱ መንጋውን ያስማራ ዘንድ ወረደ መኃ 6፡2 በማለት የምፅዓቱን ዓላማ ይገልፃል፡፡ ከርሱ በቀር ምን መሰማሪያ አለን በራችን መሰማሪያ ገነታችን ክርስቶስ ኢየሱስ ነው፡፡ ጠብቅ ማለት እርሱ ከሁለት አካል አንድ አካል ከሁለት ባህሪ አንድ ባህሪ የሆነ አምላክ ነው፡፡ ብለህ እመን ማለት ነው፡፡
በገነት ውስጥ ያሉ አፍላጋት የአራቱ ወንጌላዊያን የምስጢር ምንጭ (መገኛ ክርስቶስ መሆኑን ሲያመለክት ዕፀ ህይወትም የህይወት መገኛ እርሱ መሆኑን ያሳየናል፡፡ በዚህ ገነት ውስጥ መኖር ለሰው ህይወት ነው፡፡ ረሃብ የለም ውኃ ጥምም የለም ሀዘንና ስቃይም የለምና በዚህ ገነት ውስጥ ይኖር ዘንድ ለሁሉም ጥሪ ተላልፎአል፡፡

 

፫ኛ. እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፡- በመጽሐፍት ሁሉ መልካም ስም እና ምሳሌ የተሰጠው ከቅዱሳን ሁሉ እንደመቤታችን ማንም የለም ከነዚህ ስሞቿ መካከል ገነት የሚለው አንዱ ነው፡፡ ከነብያት አንዱ የሆነው አባቷ ሰሎሞን በዘመን ሁሉ ተጠብቆ የሚኖር ንጽሕናዋን በገለፀበት አንቀፅ ነበር፡፡ “ገነት ዕፁት ወአዘቅት ኅትምት›› መኃ 4፡12 የታተመች የውሃ ምንጭ የተዘጋች ገነት የሚል ነው፡፡ ይህንን ይዘው ከዚያም በኋላ የተነሱ ሊቃውንት እነቅዱስ ያሬድ እነ ቅዱስ ኤፍሬም ገነት ይዕቲ ነቅዓ ገነት ዐዘቅተ ማየ ህይወት የህይወት ውኃ ምንጭ የገነት ፈሳሾች መገኛ ገነት ተፈስሂ ኦ ገነት ነባቢት ማኅደሩ ለክርስቶስ የክርስቶስ ማደርያው ነባቢት ገነት አንችነሽ ፡፡ እያሉ በየድርሳናቱ አወድሰዋታል፡፡

ገነትና እመቤታችን በሚከተሉት መንገዶች ይመሳሰላሉ፡፡

  • ገነት ምስራቃዊት ቦታ ነች እመቤታችንም በምስራቃዊ የሀገራችን ክፍል የተገኘች መሆኗን ያመለክታል፡፡ አንድም የፀሐየ ፅድቅ የኢየሱስ ክርስቶስ መገኛ ናትና ነው፡፡

  • በገነት ዕፀ ህይወት ይበቅልባታል፡ ከእመቤታችንም እፀ ህይወት ተብሎ የሚጠራ ስጋውና ደሙ የመገኘቱ ምሳሌ ነው፡፡ ይህንንም ሲያስረዳ ቅዱስ ኤፍሬም ‹‹ ከእፀ-ህይወት እንበላ ዘንድ አደለን ይኸውም የክርስቶስ ስጋና ደሙ ነው ሲል ይገልጸዋል፡፡ የአማናዊት እፀ ህይወት መገኛ ድንግል አማናዊት ገነት

  • በገነት አራት አፍላጋት አሉ ብለን ነበር እነዚህ የአራቱ ንህናዎቿ ሰው የሚበድልባቸው አራት መንገዶች አሉ፡፡ ማየትና መስማት ማሽተትና መዳሰስ ናቸው ሰው በህይወት ዘመኑ በነዚህ አራት መንገዶች ሲበድል ይኖራል፡፡ እመቤታችን ግን በነዚህ ሁሉ አልበደለችውምና አራቱ የገነት አፍላጋት በእመቤታችን አራት ንፅህናዎች ይመሰላሉ ያልነው በዚህ ነው፡፡ ወንድሜ ሆይ የሚበላውን የሚጠጣውን ያስገኘችልን አማናዊት ገነት ድንግል ማርያም ናትና በርሷ ውስጥ ብትኖር ለህይወትህ መልካም ነውና ደግሜ እልሃለው ገነትን ጠብቃት፡፡

 

 

lemena 01

ንዋያተ ቅዱሳቱ የማን ናቸው?

 ጥር 26 ቀን 2006 ዓ.ም.

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የዜማ መሣሪያዎች ከቅዱስ ያሬድ ጀምሮ በርካታ ሊቃውንት ሲያገለግሉበት የነበረና የሰማያዊውን የዝማሬ ሥርዓት መነሻ ያደረገ፣ ሰማያዊውንም ዓለም የሚያሳስብ፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ቃልም መነሻ ተደርጎ የተመረጠ፣ ኢትዮጵያዊ መልክ ኖሯቸውም የተዘጋጁ ናቸው፡፡

እነዚህ የዜማ መሣሪያዎች ቤተክርስቲያናችን ይዛ በምትጠቀምበት ቅርጽና ይዘት የሚገኙት በኢትዮጵያና ኢትጵያውያን እጅ ብቻ ነው፡፡ ይልቁንም ደግሞ የአንድ ቤተ ሃይማኖት ማለትም የኦርቶዶክስ ሃይማኖት መጠቀሚያ ሆነው እያገለገሉ ያሉ ናቸው፡፡

ይህ በእንዲህ እያለ ግን ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ሌሎች ቤተእምነቶች በከበሮ፣ በመቋሚያና ጸናጽሉ በራሳቸው ተጠቅመው በራሳቸው መንገድ የራሳቸውን እምነት ሲያራምዱበት እየታየ ነው፡፡ በመድረኮቻቸው ያንን ሲያደርጉ ታይተዋል፡፡ በቴሌቪዥን ፕሮግራም ሲያስተላልፉ ተስተውሏል፡፡

በተመሳሳይ ዜማው የዝማሬ ሥርዓቱ የበዓላት ሥርዓቱ ንዋየ ቅድሳቱ ሁሉ ደረጃ በደረጃ በተለያዩ ቤተእምነቶች ቁጥጥር ሥር ወድቋል፡፡ የበዓላት ቀናቱ ጭምር በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ባሕረ ሐሳብ መሠረት የሚወጣ ቢሆንም እንደራሳቸው አደርገው በዓል ሲያደርጓቸው ልዩ ልዩ መርኀ ግብር ሲፈጸምባቸው ይታያል፡፡ ለዚህ ማሳያ የሚሆነው የመስቀል በዓል ነው፡፡ በዓለ መስቀል ኦርቶዶክሳውያንን ብቻ የሚመለከት በዓል ቢሆንም አሁን ግን በቤተክርስቲያኒቱ የበዓል ዐውድ ውስጥ ሌሎች ቤተእምነቶች የራሳቸውም እንደሆነ በሚያስመስል መንገድ ስለሚቀርቡ ግራ መጋባት እየፈጠረ ነው፡፡ ይሄ ነገር በዚሁ ከቀጠለ ቤተክርስቲያናችን የእኔ የምትለው የራሷ ነገር እየጠፋ ሊመጣ ይችላል፡፡

በመሆኑም የዝግጅት ክፍላችን በተለይ የዜማ መሣሪያ በሆኑ ንዋየ ቅድሳት ጋር በተያያዘ ሁለት ባለሙያዎችን ለማነጋገር ጥረት አድርጓል፡፡ ያነሣናቸው ጥያቄዎችም ከሕግ፣ ከቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ አንጻር በመሆኑ ያነጋገርናቸው ባለሙያዎችም በእነዚሁ ጉዳዮች ላይ ባለሙያ የሆኑ ናቸው፡፡ እነሱም የሕግ ባለሙያ የሆኑት አቶ ጌታሁን ወርቁና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑት መምህር መንግሥቱ ጎበዜ ናቸው፡፡ ሁለቱንም ባለሙያዎች ጠይቀን የሰጡንን መልስ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡

 

ሐመር፡- አንዱ ቤተእምነት የሌላውን ቤተእምነት የትኛውንም ዓይነት የአገልግሎት መጠቀሚያ ንዋየ ቅድሳት መጠቀሙ ሕጋዊ ሊሆን የሚችልበት አካሔድ አለ? ሌሎች ከዚህ ጋር ተያያዥ የሆኑ የሕግ ሐሳቦችን ቢያመለክቱን

lemena 01አቶ ጌታሁን ወርቁ፡– የቤተእምነት አገልግሎት መጠቀሚያን በተመለከተ ያሉት ሕግጋት በጣሙን ግልጽነት የሚጎድላቸው ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ከተመሠረተችበት ጊዜ ጀምሮ የምትጠቀምባቸው ንዋየ ቅድሳት አሉ፡፡ እነዚህን ንዋየ ቅድሳት ሌሎች ቤተእምነቶች ሲጠቀሙ አስተውያለሁ፡፡ እናም ጥያቄው የመጠቀማቸው ሁኔታ ከምን ሕግ የመነጨ ነው፡፡ ወይም ቤተክርስቲያኗ ንዋየ ቅድሳቱን ራሷ ብቻ እንድትጠቀም የማድረግ መብት ይኖራታል ወይ የሚለው ነው ምላሽ የሚፈልገው ጭብጥ፡፡
በሕግ አንድ ሰው የተፈጥሮ ወይም በሕግ ሰውነት የተሰጠው ተቋም መብት ሊያገኝ የሚችለው ከሕግ አልያም ከውል ነው፡፡ የቤተክርስቲያኗን መብት ሕግ እውቅና ከሰጠውና ስፋትና ወሰኑን ካስቀመጠው መብቷን ለመጠየቅ መነሻ ይሆናል፡፡ ሁለተኛው ውል ሲሆን ሁለት ወይም ከዛ በላይ የሆኑ ሰዎች (ተቋማት) መብቶችንና ግዴታዎችን ለማቋቋም ለማሻሻል ወይም ለማቋረጥ የሚያደርጉት ስምምነት ነው፡፡ እንዲህ ዓይነት ስምምነት በነፃ ፈቃድና በችሎታ ከተደረገ፤ ከሕግና ከሞራል ተቃራኒ ካልሆነ በተዋዋይ ወገኖች መካከል ሕግ ሆኖ የሚያስገድዳቸው ይሆናል፡፡

ንዋያተ ቅድሳትን በተመለከተ በቅድሚያ ግልጽ መሆን ያለባቸው የብያኔና በልማድ የሚታዩ ነጥቦች አሉ፡፡ የመጀመሪያው የንዋያተ ቅድሳት ትርጉም ነው፡፡ ከቃሉ ጥሬ ትርጉም ብንነሳ ንዋያተ ቅድሳት የሚባሉት ለእግዚአብሔር አምልኮ መፈፀሚያ የሚሆኑ ዕቃዎች ናቸው፡፡ በቤተክርስቲያን ትምህርት እነዚህን ንዋያት በቅዱስ ሜሮን የሚከብሩ ለዜማ፣ ለቅዳሴ፣ለምስጋና የተለዩ ዕቃዎች ናቸው፡፡ እነዚህን ንዋያት በተመለከተ ቤተክርስቲያን ብዙም አከራካሪ ያልሆነ መብት አላት፡፡ በተግባርም እነዚህ ንዋያት ሲሰረቁ፣ ሲዘረፉ ወዘተ ለፖሊስና ለፍ/ቤት አቤቱታ በማቅረብ ስታስመልስ የቆየችው ከዚሁ በመነሳት ነው፡፡ በሌላ በኩል ግን በቅዱስ ሜሮን የከበሩም ቢሆን የንዋያተ ቅድሳት ስፋት ከመስቀሉ፣ ከበሮ ጀምሮ ጧፍና እጣንም ሳይቀሩ የሚካተቱበት ነው፡፡ ጧፍ በየቦታው ከመመረቱና ለተለያዩ ማኅበራዊ አገልግሎት ከመዋሉ አንፃር በቅዱስ ሜሮን ቢከብርም እንደሌሎች ንዋያት ጠንካራ የሕግ ጥበቃ ላይሰጠው ይችላል፤ ይህም የሆነው ከማስረጃ አስቸጋሪነት አንጻር ነው፡፡ በቅዱስ ሜሮን ከብረው ንዋያተ ቅድሳት ያልሆኑት ግን የተለየ ምልከታ ሊደረግላቸው ይገባል፡፡ በሜሮን ባይከብሩም በቤተክርስቲያኗ ለዘመናት አምልኮ፣ ምስጋና ለመፈጸም ግብዓት የሚሆኑ ዕቃዎችን ለምሳሌ ከበሮ፣ ጸናጽል፣ መቋሚያ፣ ጥንግ ድርብ ወዘተ የመሳሰሉትን መሳሪያዎች በተመለከተ ግን ቀደም ሲል ያየናቸውን ያህል ግልጽ የሕግ ጥበቃ ሥርዓት አለመኖሩን አምናለሁ፡፡

በሕግ ደረጃ ለቤተክርስቲያኗ መብት መነሻ የሚሆኑት በፍትሐ ብሔር ሕጉ የተደነገገው የንብረት ሕግ፣ ስለቅርስ ጥናትና አጠባበቅ የወጣው አዋጅ እንዲሁም የቅጅና የተዛማጅ መብቶች ጥበቃ አዋጅ ናቸው፡፡ በእነዚህ ሕግጋት ቤተክርስቲያኗ በሕግጋቱ ላይ መብቷ እንዲታወቅና እንዲጠበቅ የተደነገጉትን ሁኔታዎች ካሟላች ባለመብት ሆና ሌሎች እንዳይጠቀሙ የምትከላከልበት ሁኔታ ይኖራል፡፡

በንብረት ሕግ በንብረት ላይ ሰፊ ጥበቃ የሚሰጠው መብት የሀብትነት (ባለቤትነት) (Ownership) መብት ሲሆን ይህ መብት በንብረቱ የመገልገል፣ ንብረቱን ለሌላ መጠቀሚያ የማከራየት ወይም የመሸጥ የመለወጥ መብትን ያጠቃልላል፡፡ በአንድ ዕቃ ላይ የባለቤትነት መብት ያለው ሰው /ተቋም መብት ሳይኖረው እጁ ካደረገው ሰው ወይም ከያዘው ሰው ሀብቱ ይገባኛል ሲል ለመፋለምና ማናቸውንም የኃይል ተግባር ለመቃወም እንደሚችል በፍትሐ ብሔር ሕግ ቁጥር 1206 ተደንግጓል፡፡ በሕጉ ባለሀብትነት (ባለቤትነት) የሚረጋገጠው እንደ ንብረቱ ዓይነት ነው፡፡ የሚንቀሳቀስ ግዙፍ ነገር ባለይዞታ የሆነ ሰው በራሱ ስም እንደያዘውና የዚሁ ነገር ባለቤት/ባለሀብት/ እንደሆነ ይገመታል ሲል ሕጉ በ/ፍ/ብ/ሕ/ቁ 1193 ደንግጓል፡፡ በዚህ ድንጋጌ መሠረት ተራ ተንቀሳቃሽ (Ordinary Corporeal chattels) ባለቤትነት እጅ በማድረግ (በመያዝ) ብቻ ባለቤት ይኮናል፡፡ ሆኖም ሕጉ በልዩ ሁኔታ ልዩ ተንቀሳቃሽ ንብረት በመባል የሚጠሩትን መኪናን የመሰሉትን የምዝገባ መስፈርቶች በልዩ አዋጅ በማስቀመጡ ንብረቱን በእጅ ከማድረግ ባለፈ ካልተመዘገበ የባለቤትነት መብት አያስገኝም፡፡ ሁለተኛው የባለቤትነት ማረጋገጫ የማይንቀሳቀስ ንብረትን የሚመለከት ሲሆን በአስተዳደር ክፍል ባለቤትነቱ ታውቆና ተመዝግቦለት የባለሀብትነት የምስክር ወረቀት የተሰጠው ሰው /ተቋም የንብረቱ ባለቤት ይሆናል፡፡

ንዋያተ ቅድሳትን በተመለከተ (በቅዱስ ሜሮን ያልከበሩትን) የተለየ ሕግ ባለመኖሩ ልዩ ተንቀሳቃሽ ንብረት በሚለው የማይወድቁና የምዝገባ ሥርዓት ያልተመዘገበላቸው ናቸው፡፡ ስለዚህ እነዚህ ዕቃዎች ከገበያው በሽያጭና በስጦታ የሚገኙና የገዛቸው ሰው ባለሀብት (ባለቤት) የሚሆንባቸው በመሆኑ ሁሉም ቤተ-እምነት የዕቃዎቹ ባለቤት የመሆን እድላቸው የተዘጋ አይደለም ማለት ነው፡፡ በዚህ መነሻነት ቤተክርስቲያን የራሷን ንዋያት መጠበቅ፣ ሌላው እንዳይጠቀም የማድረግ መብት ያላት ንዋያተ ቅድሳቱ በእጇ ገብተው እየተጠቀመችባቸው ካሉ ብቻ ይሆናል፡፡

ሁለተኛው ለመብት አጠባበቅ መሠረት የሚሆነው ስለቅርስ አጠባበቅ የወጣው አዋጅ ቁጥር 209 /1992 ዓ.ም ነው፡፡ በዚህ አዋጅ ትርጓሜ መሠረት “ንዋየ ቅድሳት” በአንቀጽ 2(6) “ግዙፍነት ያለው ቅርስ ” በሚለው ምድብ ይወድቃሉ፡፡ ግዙፍነት ያለው ቅርስ ማለት በእጅ የሚዳሰሱ፣ በዓይን የሚታዩ የሚንቀሳቀሱና የማይንቀሳቀሱ ባህላዊና ታሪካዊ ወይም ሰው ሠራሽ ቅርሶችን ይጨምራል፡፡ “የማይንቀሳቀስ ቅርስ” ውስጥ የብራና ጽሑፍ ከወርቅ ፣ ከብር፣ ከነሐስ፣ ወይም ከብረት ወይም ከመዳብ ከሌሎች ንጥረ ነገሮች ከእንጨት፣ ከድንጋይ፣ ከቆዳ፣ ከዝሆን ጥርስ፣ ከቀንድ፣ ከአጥንትና ከአፈር ወይም ከሌሎች ነገሮች የተሰሩ ቅርሶችና ምስሎች ይገኙበታል፡፡ በዚህ ብያኔ መሠረት የቤተክርስቲያን ንዋያተ ቅድሳት የሚንቀሳቀሱ ቅርሶች ናቸው፡፡ በዚህ አዋጅ አንቀጽ 14 መሠረት ቤተ ክርስቲያን የንዋያተ ቅድሳቶቿ ባለቤት መሆን የምትችል ሲሆን ንዋያተ ቅድሳቱ በቅርስ ጥበቃ ባለሥልጣን ተመዝግበው የሕግ ጥበቃ ይሰጣቸዋል፡፡ ቤተክርስቲያን በዚህ አዋጅ መሠረት ያስመዘገበቻቸው ቅርሶች ከመሠረታዊ ዓላማቸው፣ ከታሪካዊ አመጣጣቸውና ሊሰጣቸው ከሚገባው ክብር ዝቅ የሚያደርጉ ተግባራትን ለቅርስ ባለሥልጣን ሪፖርት በማድረግ የንዋያተ ቅድሳቱን አጠቃቀም ጥበቃ እንዲደረግ ለመጠየቅ ትችላለች፡፡

የመስቀል በዓል አከባበር በዓለም ቅርስነት የመመዝገቡ እውነታ ደግሞ ለቤተክርስቲያኗ ተጨማሪ ጥበቃ እንደሚ ያስገኝላት ይታሰባል፡፡ የመስቀል በዓል ምዝገባ ባህላዊና ሃይማ ኖታዊ ሥርዓቶችን አካትቶ የተመዘገበ በመሆኑ ሃይማኖታዊ በሆኑት መጠን ቤተክርስቲያኗ ከምዝገባው መብት ታገኛለች፡፡ ንዋያተ ቅድሳቱ (አለባበሱ፣ ዝማሬው፣ ንዋያተ ቅድሳቱና ውሕደታቸው) በምዝገባው መሠረት በተመሳሳይና በወጥነት ሳይበረዙ እንዲተላለፉ የማድረግ መብት አላት፡፡ ይህ መብት ሥርዓቱን እንዳመጣበት እንዳይቀጥል የማድረግ ውጤት ያላቸውን የአለባበስ፣ የዝማሬ፣ ወይም የንዋያተ ቅድሳት አጠቃቀም እንዲከላከል ለኢትዮጵያ መንግሥት ወይም ለዩኔስኮ እስከማቅረብ እንደሚደርስ መረዳት ይችላል፡፡

ሦስተኛው ለመብት ጥበቃው መሠረት የሚሆነው የቅጅና ተዛማጅ መብቶች ጥበቃ አዋጅ ቁጥር 410/1996 ዓ.ም ነው፡፡ በዚህ አዋጅ መሠረት ንዋያተ ቅድሳቱ በራሳቸው ተለይተው ሳይሆን ከዝማሬ፣ አቋቋም፣ ቅዳሴ ወ.ዘተ ጋር ተዋሕደው ሕጉ ጥበቃ ሊያደርግላቸው ይችላል፡፡ ለምሳሌ ከበሮ፣ መቋሚያ፣ ጸናጽል ከዜማው ጋር በቅኔ ማኅሌት የሚደረገው ክንውን (Performance) መብት ጥበቃ ሊያገኝ ይችላል፡፡ በዚህ አዋጅ መሠረት ጥበቃ ለማግኘት የዜማ ሥራው ወጥ (Original) እንዲሁም የተቀረጸ ወይም ግዙፍነት ያገኘ ሊሆን ይገባዋል፡፡ ይህም ማለት ሥራው ለሕዝብ የቀረበ ወይም የታተመ መሆን አለበት፡፡ በዚህ ረገድ ቤተክርስቲያን ያሉዋትን የንዋያተ ቅድሳት አጠቃቀም በተመለከተ በሚወጡ ቪዲዮዎች፣ ለሕዝብ ሲቀርብ፣ ተቀርጾ ሲተላለፍ ወዘተ ሌሎች በታየው /በቀረበው/ በታተመው መሠረት የንዋያተ ቅድሳቱን ውሕደት እንዳይጠቀሙ የመከላከል መብት ይኖራታል፡፡ ይህ መብት በአብያተ ክርስቲያናቱ ወይም በግለሰብ አማኞች (ማኅበራት፣ ግለሰብ ዘማርያን ወዘተ) ሊጠየቅ ይችላል፡፡

ከላይ በመግቢያው እንደገለጽኩት ሁለተኛው የመብት ምንጭ ውል ሲሆን በሃይማኖት ተቋማት ስለአምልኮ አፈፃፀም፣ ስለአማኞች ስርቆት (Sheep stealing)፣ አንዱ የሌላውን የአምልኮ መፈጸሚያ፣ የአምልኮ ዕቃን ስለመጠቀም አለመጠቀም፤ የጋራ የሆኑ ጉዳዮች ላይ በአንድነት ስለመሥራት የተደረገ ስምምነት ካለ ይህ ገዥ መሆኑ አይቀርም፡፡ እንደሚ ታወቀው በክርስትና ስም ያሉ ቤተ-እምነቶች የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት አባል በመሆናቸው እርስ በርሳቸው ባላቸው ግንኙነት አንዱ ሌላውን የሚጎዳ ድርጊት እንዲሠራ የማይፈቅዱበት ሁኔታ ይኖራል፡፡ እምነት በልብ የሚታመን ብቻ ሳይሆን በአፍ የሚነገር በድርጊት የሚገለጥ ነው፡፡ አለባበስ፣ ዝማሬ፣፣ በተለያዩ ንዋያተ ቅድሳት በመጠቀም አምልኮ መፈፀም የእምነቱ አካል ነው፡፡ አንዱ ቤተ እምነት የሌላውን ፈቃድ ሳያገኝ ለዘመናት ሲጠቀምበት የነበረውን የአምልኮ መፈፀሚያ የሚጠቀም ከሆነ በኅብረት የመኖራቸው ነገር ትርጉም ያጣል፡፡ አንዱ የሌላውን የሆነውን ሀብት፣ ትውፊት ያለፈቃድ የሚወስድ ከሆነ አብያተ ክርስቲያናቱ በጋራ የገቡትን ውል ወይም ስምምነት መጣስ ነው፡፡ ይህ መብቱ የተጣሰበት ቤተ-እምነት ስምምነቱን መሠረት በማድረግ መብቱ እንዲከበርለት የመጠየቅ መብት ይኖረዋል ማለት ነው፡፡ ሙሉ/ ስምምነቱ በአብያተ ክርስቲያናቱ መካከል እንደ ሕግ ስለሚቆጠር መብቱ ለተጣሰበት ቤተ እምነት መፈጸሙ መፍትሔ /Remedy/ እንደሚሆን ማሰብ ይቻላል፡፡

እስካሁን የተመለከትነው ከንብረት መብትና ከቅርስ አንጻር ያለውን የመብትና ግዴታ አተያይ ነው፡፡ አንዱ ቤተእምነት አምልኮውን ከሚፈጽምበት መጠቀሚያ አንጻር መብቱ የሚሰጠው ስለመሆኑ ነው፡፡ በሌላ በኩል ግን በቤተ እምነቶች መካከል አምልኮን ከመፈጸሚያ ዕቃ (መሣሪያ) አንጻር የሚነሱ አለመግባባቶችም ከእምነት ነጻነትና ከሕዝብ ደኅንነት አንጻር ሊታይ ይችላል፡፡ አንዱ ቤተእምነት የሌላውን ቤተእምነት ሀብት ወይም የአምልኮ መሣሪያ መጠቀሙ ለዘመናት ሲጠቀምበት የነበረውን የቤተ እምነት ተከታዮች ቅር የሚያሰኝ ወይም ቁጣ የሚያስነሳ ሊሆን ይችላል፡፡ እንዲህ ዓይነት ጉዳዮች በእኛ ሀገር የሕግ ሥርዓት መፍትሔ የሚያገኙት ደግሞ የእምነት ነፃነትን ጥበቃ የሚሰጠው ሕገ መንግሥቱ ወይም ከሕዝብ ደኅንነትና ሰላም መጠበቅ በወጣው የወንጀል ሕጉ ነው፡፡ በዚህ ረገድ ሁለቱን ሕግጋት ከተነሳንበት አንፃር መፈተሸ ተገቢ ይሆናል የሚል እምነት አለኝ፡፡

የሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 27(1) “የሃይማኖት፣ የእምነትና የአመለካከት ነፃነት በሚል ርዕስ” ማንኛውም ሰው የማሰብ የሕሊና እና የሃይማኖት ነፃነት አለው፡፡ ይህ መብት ማንኛውም ሰው የመረጠውን ሃይማኖት ወይም እምነት የመያዝ ወይም የመቀበል ሃይማኖቱንና እምነቱን ለብቻ ወይም ከሌሎች ጋር በመሆን በይፋ ወይም በግል የማምለክ የመከተል የመተግበር፣ የማስተማር ወይም የመግለጽ መብትን ያካትታል» ሲል ይደነግጋል፡፡

ይህ ሕገመንግሥታዊ ድንጋጌ ለሃይማኖት ነፃነት ዋስትና የሚሰጥ ቢሆንም የሃይማኖት ነፃነት ገደብ የለውም ማለት አይደለም” የሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 27(5) “ሃይማኖትንና እምነትን የመግለጽ መብት ሊገደብ የሚቻለው የሕዝብን ደኅንነት፣ ሰላምን፣ ጤናን፣ ትምህርትን፣ የሕዝብን የሞራል ሁኔታ፣ የሌሎች ዜጎችን መሠረታዊ መብቶችና ነፃነቶች እና መንግሥት ከሃይማኖት ነፃ መሆኑን ለማረጋገጥ በሚመጡ ሕጎች ይሆናል” በማለት ደንግጓል፡፡ በዚህ ድንጋጌ መሠረት የሚገደበው የሃይ ማኖት መብት / የመረጡትን እምነት መያዝ ሳይሆን አገላለጹ ነው፡፡ የእምነት /አመለካከት/ መብት ፍጹማዊ በመሆኑ አይገደብም፣ መገደብም አይቻልም፡፡ ሃይማኖትን የመግለጽ መብት ለሕዝብ ሰላምና ደኅንነት ሲባል ገደብ ሊጣልበት ይችላል፡፡ የአንድ እምነት የአምልኮ ሥርዓቶች ኅብረተሰቡን የሚረብሹ፣ የሕዝብን ሥርዓትና ደኅንነት የሚያናጉ፣ በኅብረተሰቡ ሕይወት፣ ህልውና እና ንብረት ላይ ከባድ አደጋ የሚያደርሱ ሆነው ከተገኙ መንግሥት ሕግ ማውጣት እና ገደቡም በአግባቡ እንዲመራ በማድረግ ገደብ ሊጥል ይችላል፡፡

በቤተ እምነት መካከል የሚታየው የአንዱን የአምልኮ መፈፀሚያ መሳሪያ ሌላው ያለፈቃዱ የመጠቀሙንም ነገር እኔ የማየው ከእምነት አገላለጽ ነው፡፡ አንዱ ቤተእምነት ለዘመናት ሲዘምርበት፣ ሲያመሰግንበት የቆየበትን ሥርዓት እና የአገልግሎት መጠቀሚያ ሌላው ሲጠቀም በአማኞቹ መካከል አለመግባበት ይከሰታል፡፡ እምነቱ በኅሊና ብቻ ያለ ሳይሆን አማኙ የሚለብሰውም፣ የሚዘምረውም፣ የሚጠቀምበትን የንዋያተ ቅድሳት ዓይነት የሚያካትት ነው፡፡ ስለዚህ የራሱ ባልሆነው የተጠቀመው ቤተ እምነት የሌላውን ቤተእምነት መብት የሚነካ ነው፡፡ እንዲህ ባለ ጊዜ ታሪክን፣ የቤተ እምነቶቹን ሥርዓት፣ የዳበረ ልማድን መሠረት አድርጎ ክልከላ ካልተደረገበት ሥርዓት አልበኝነት ይነግሣል ለሕዝቡም ሰላምና ደኅንነት ስጋት መሆኑ አይቀርም፡፡ ስለዚህ መንግሥት በሕገ መንግሥቱ በግልጽ የተቀመጠውን የሃይማኖት ነፃነት ገደብን መሠረት በማድረግ ቤተእምነቶች መካከል የሚታየውን አንዱ አንዱን የማንቋሽሽ ድርጊት፣ የአንዱን ቤተእምነት የአምልኮ መጠቀሚያ ያለአግባብ መጠቀምን የመሰሉ በሕዝቡ ውስጥ ረብሻና ሁከት የመፍጠር አቅም ያላቸውን አሠራሮች መስመር ሊያስይዝ ይገባል፡፡ ይህ አካሄድ የሃይማኖት ብዙኅነትንም የሚያስቀር እና የአማኞችን ማንነት በማያሻማ መልኩ እንዲገለጽ የማያደርግ በመሆኑ የሕጉ ጣልቃ ገብነት አስፈላጊ ነው፡፡ በአንዳንድ ሀገራት እንኳን የሃይማኖት መገለጫው (የአምልኮ መሳሪያው) የቃላት አጠቃቀም እንኳን የሕግ ጥበቃ ይሰጠዋል፡፡ ቢቢሲ በድረገጹ እ.ኤ.አ ኦክቶበር 14 ቀን 2013 እንደዘገበው የማሌዥያ ፍርድ ቤት ከሙስሊም እምነት ውጭ ያሉ እምነቶች “አላህ” የሚለውን ቃል መጠቀም እንደማይችሉ ፍርድ ሰጥቷል፡፡ ለፍርዱ መነሻ የተደረገው አመክንዮ ቃሉ ከሙስሊም እምነት ውጭ ያሉ እምነቶች ጥቅም ላይ ቢውል ሕዝባዊ ሥርዓት አልበኝነት (Public disorder) ስለሚያስከትል ነው፡፡ ቴሌግራፍ የፍ/ቤቱን ተጨማሪ ምክንያት ሲገልጹ “The usage of the word will cause confusion in the community” በማለት ዘግቦታል፡፡ የዚህ ፍርድ የፍትሃዊነት ክርክር እንደተጠበቀ ሆኖ ከዚህ ፍርድ በመነሣት የተነሳንበትን ጉዳይ ከመረመርነው የአንዱን ቤተ እምነት የእምነት መፈጸሚያ ሥርዓትና መሳሪያዎች መጠቀም በኅብረተሰቡ ውስጥ የሚመጣውን መደናገርና በማንነት ፍለጋ (ጥበቃ) ሊከተል የሚችለውን ሁከት ማሰብ አስቸጋሪ አይሆንም፡፡

ሕገ መንግሥቱን መሠረት አድርጎ የወጣው የወንጀል ሕግም በተለይ በአደባባይ የሚፈጸሙ የሃይማኖት ሥርዓትን የሚያውክ፣ ወይም ያስተሃቀረን ሰው የሚቀጣ ድንጋጌ አለው፡፡ ሕጉ በአንቀጽ 792 “የሃይማኖት ሰላምና ስሜት መንካት በሚል ርዕስ” ማንም ሰው አስቦ በአደባባይ፡-

ሀ) የተፈቀደውን ሃይማኖታዊ ሥርዓት፣ ሥነ በዓል ወይም ሃይማኖታዊ ተግባር እንዳይፈፅም የከለከለ፣ ያወከ ወይም ያስተሐቀረ እንደሆነ፤ ወይም

ለ) ለሃይማኖታዊ ሥነሥርዓት ብቻ የሚያገለግለውን ቦታ፣ ሥዕል፣ ወይም ዕቃ ያረከሰ እንደሆነ

ከአንድ ሺሕ ብር በማይበልጥ መቀጮ ወይም ከሁለት ዓመት በማይበልጥ ቀላል እስራት ይቀጣል፡፡” ሲል ይደነግጋል፡፡

በዚህ ድንጋጌ መሠረት ‹‹ንዋየ ቅድሳት›› በ “ለ” ለሃይማኖት ሥነ ሥርዓት ብቻ የሚያገለግል ዕቃ” በሚል የሚሸፈኑ ሲሆን እነዚህን ዕቃዎች ‹ያረከሰ› በሕግ ተጠያቂ እንደሚሆን ይደነግጋል፡፡ ‹ያረከሰ› የሚለው ቃል ለዳኞች ትርጉም የተተወ ቢሆንም ከቃሉ ጥሬ ትርጉም ‹ከዓላማው ውጭ የተጠቀመ፣ ከእምነቱ ሥርዓት ያፈነገጠ ወ.ዘ.ተ» አጠቃቀም እንደሚመለከት መገንዘብ አከራካሪ አይሆንም፡፡ ለአብነት በክርስትና ቤተእምነቶች መካከል ያለውን የዶግማና የቀኖና ልዩነት ላስተዋለ ንዋየ ቅድሳቱን (ከበሮውን፣ ጸናጽልና መቋሚያውን› በታሪክ በትውፊት በቆየ ልማድ ከሚጠቀምበት ቤተ እምነት ዓላማ፣ ሥርዓትና አሠራር ውጭ መጠቀም ተገቢ አለመሆኑን መረዳት ይቻላል፡፡ ድርጊቱ በወንጀል ሕጉ የሚያስቀጣ ከሆነ ለማንኛውም ቤተ-እምነት ተከታይ የሌላውን ሥርዓት፣ ትውፊት እና አምልኮ መሣሪያ የመጠቀሚያ መብት እንደማይኖር መገንዘብ ይቻላል፡፡

ሐመር፡- ቤተ ክርስቲያኗ እንዴት የንዋየ ቅድሳቷን ይዞታ ታስከብር?

አቶ ጌታሁን ወርቁ፡- ከላይ እንደተመለከትነው የቤተክርስቲያን ንዋያተ ቅድሳት በሌሎች ቤተ-እምነቶች እየተጠቀሙ መቀጠል የራሱ የሆነ አሉታዊ ውጤት እንዳለው መገንዘብ ከባድ አይደለም፡፡ የቤተ እምነቷ መብት መነካት፣ አማኙ ወደ አልተፈለገ ሁከትና ክርክር መግባት፣ በቤተ እምነት መካከል የጥላቻ ስሜት መዳበር ወ.ዘ.ተ ያልተፈለጉ ውጤቶች ናቸው፡፡ ይህን ለማራቅ ቤተክርስቲያኗ የራሷን ንዋያተ ቅድሳት መጠበቅ አለባት፡፡ ከቤተክርስቲያኗ የሚጠበቀውን ለመመልከት ያህል ቢያንስ ሦስት መፍትሔዎች መጠቆም ይቻላል፡፡

የመጀመሪያው ቤተክርስቲያኗ የራሷን ንዋየ ቅድሳት መለየት፣ መቁጠርና መመዝገብ ነው፡፡ ንዋያት ቅድሳቱን በተመለከተ ታሪካቸውን፣ አመጣጣቸውን፣ ትርጉማቸውን ወ.ዘ.ተ በማጥናት የመለየትና ከመመዝገብ ጋር ትውፊታቸውን እንዲጠብቁ በመቅረጽ (በፎቶ፣ በቪዲዮ ወ.ዘ.ተ) ማተም እና ማሳወቅ ይጠበቅባታል፡፡ እነዚህን ድርጊቶች መከወኗ በአንድ በኩል በቅርስነት ለማስመዝገብ (በሀገር ውስጥም በዓለም አቀፍ ደረጃም) የሚጠቅማት ሲሆን በተጨማሪ በንብረት ሕግ፣ በቅጅና ተዛማጅ መብቶች ጥበቃ አዋጅ መብቷን ለመጠቀም ያስችላታል፡፡

ሁለተኛው መብት የመጠየቅ ሥራ ነው፡፡ ከላይ እንደተመ ለከትነው አንዳንዶቹ ሕግጋት ያለፈቃድ የሌላ ቤተእምነትን ሥርዓትና የአምልኮ መገልገያ እቃዎችን መጠቀምን በአንድም በሌላ ይከለክላሉ፡፡ እንዲህ ዓይነት ድርጊት የሚፈጽሙ ቤተ እምነቶችን በውይይት፣ ካልሆነም በዓለምአቀፍ የአብያተ ክርስቲያናት ኅብረት በኩል መጠየቅ የማይጎረብጥ መፍትሔ ነው፡፡ ከዚህ መፍትሔ ጎን ለጎን ቤተክርስቲያኗ እንደ አግባብነቱ መብቶቿን ከፖሊስ፣ ከመንግሥት (ከፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር)፣ ከኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ጽ/ቤት ወይም ከፍ/ቤት መጠየቅ ትችላለች፡፡

የመጨረሻው ቤተ ክርስቲያኗ ከመንግሥት ጋር በምታ ደርገው ትብብር የሚገኝ መፍትሔ ነው፡፡ ንዋየ ቅድሳትን በሌላ ቤተ እምነት የመጠቀም ድርጊት በዋናነት ሊቆም የሚችለው መንግሥት በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 27 (5) መሠረት የእምነት ነፃነት አገላለጽ ገደብን በሕግ ወይም በመመሪያ መደንገግ ሲችል ነው፡፡ ቤተክርስቲያኗ በቤተ እምነቶች መካከል በዜማ፣ በንዋየ ቅድሳት፣ ወ.ዘ.ተ ጋር በተያያዘ የሚደረጉ ገደቦች የሀገሪቱን ታሪክ፣ ለዘመናት በኅብረተሰቡና በቤተእምነቶቹ የዳበረውን ልማድ ትውፊትና መቻቻል መሠረት ማድረግ እንደሚገባው በመገንዘብ መንግሥት ገደቦቹን በተግባር እንዲተረጉማቸው መጠየቅ ይገባል፡፡ መመሪያውን ወይም ደንቡን ወይም ሕጉን የማውጣት ግዴታ በዋናነት የመንግሥት ቢሆንም ቤተክርስቲያኗ ሕጉ እንዲወጣ ግፊት ማድረግ፣ ከመንግሥትና ከቤተእምነቶች ጋር መተባበር ይጠበቅበታል፡፡ ይህ ግፊት “ሳይቃጠል በቅጠል” እንዲሉ በቀጣይ በስፋት ሊመጡ የሚችሉና የመቻቻልን መርህ የሚቃረኑ የቤተ- እምነት ድርጊቶች እንዳይኖሩ የራሱን አስተዋጽኦ ያደርጋል፡፡

 

ሐመር-የመዝሙር መገልገያ መሣሪያዎችን ጨምሮ ንዋየ ቅድሳት ከቅርስነት አንጻር ያላቸው ቦታና ጥቅም ምንድነው?

መንግሥቱ ጎበዜ፡- ቅርሶች የሰው ልጆች በየዘመናቸው መንፈሳዊ አእምሮአቸውን ለማርካት፣ መሠረታዊ ኑሯቸውን ለማሟላትና ሥነ ልቦናዊ ፍላጎቶቻቸውን ለማሳካት ሲሉ ለረጅም ዘመናት ከአካባ ቢያቸው ጋር በነበራቸው ግንኙነት ያከናወ ኗቸው የሥራና የፈጠራ ውጤቶች ናቸው፡፡ ከእነዚህም መካከል ለሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያ ይጠቀሙባቸው የነበሩ ክቡር ዕቃዎች በዋናነት ይጠቀሳሉ፡፡ እነዚህም የከበሩና ውድ ሀብቶች ባላቸው ታሪካዊና ባህላዊ ጠቀሜታ፣ ሥነ ጥበባዊ ይዘት፣ ያላቸው ፋይዳ፣ ምልክታዊነትና ናሙናነ ታቸው እንዲሁም ዕድሜያቸው ታይቶ ቅርስ ተብለው ለመጠራትና ለመታወቅ የሚችሉት ናቸው፡፡

ከዚህ አንጻር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት፣ መምህራንና ምእመናን በየዘርፉ ሠርተውና ጠብቀው ለትውልድ ያስተላለፏቸው ቅርሶች በዓይነትም በብዛትም የትየለሌ ናቸው፡፡ ከእነዚህም መካከል የያሬዳዊ መዝሙር መሣሪያዎች ይጠቀሳሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ ለዘመናት ጠብቃ ያቆየቻቸው እነዚህ ቅርሶች ሥርዓተ አምልኮን በሚገባ ለማከናወን፣ ትምህርተ ሃይማኖትን ለማስተላለፍ፣ መንፈሳዊ በረከት ለማግኘትና ለመሳሰሉት ሃይማኖታዊ አገልግሎት የሚውሉ ናቸው፡፡

ከመንፈሳዊ አገልግሎት ሌላ በቤተ ክርስቲያን የሚገኙ ቅርሶች የታሪክ ምስክር፣ የመረጃ ምንጭ፣ የማንነት መገለጫ፣ ዘርፈ ብዙ ዕውቀት የሚሰጡ ትምህርት ቤቶች፣ የልማት መሠረትና የምጣኔ ሀብት የጀርባ አጥንት፣ ዘመናትን የሚያተሳስሩ ድልድዮች፣ የሩቁን አቅርበው የራቀውን አጉልተው የሚያሳዩ መነጽሮች፣ የራስን ማንነት የሚያሳዩ መስታወቶች፣ በተገቢው ሁኔታ ለመኖር የሚያስችሉ የጥበብ መንገዶች፣ የአገርን መልካም ገጽታ ለመገንባት የሚያግዙ የዲፕሎማሲ አውታሮች፣ በመረጃ ላይ ውሳኔ ለመስጠት የሚያስችሉ ጠቃሚ ሰነዶች እና የሀገር አንድነት ግንባታ የማኅበረሰብ ትስስር መሠረቶች ናቸው፡፡

ሐመር-አንዱ ቤተእምነት የሌላውን ንዋየ ቅድሳት ለአገልግሎቱ መጠቀሙ እንደ ራሱ አድርጎ በአደባባይ የመጠቀሙ ልማድ ከቅርስ ጥበቃ አንጻር የሚያስከትላቸው ችግሮች ካሉ ቢያመለክቱን

መንግሥቱ ጎበዜ፡- በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክርስቲያን ቅርሶች ዙሪያ በርካታ ችግሮች የሚታዩ ሲሆን ከእነዚህም መካከል በቅርስ ባለቤትነትና የይዞታ መብት ላይ ከሌሎች አካላት ጋር የሚያወዛግብና የቤተ ክርስቲያን ቅርሶች ይጠቀሳሉ፡፡ ከዚህ አንጻር የብራlemena 02 መጻሕፍትና ለአክብሮተ ቁርባን የሚውሉ ንዋያተ ቅድሳት በሌሎች የእምነት ተቋማት አገልግሎት ሲሰጡ ይስተዋላሉ፡፡ በመሠረቱ የቤተ ክርስቲያን ቅርሶች ከቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ፣ ሥርዓተ እምነትና ትውፊት ጋር ከፍተኛና ቀጥተኛ የሆነ ቁርኝት ስላላቸው በሌሎች ቦታ አገልግሎት ላይ መዋላቸው አግባብ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ይህ ሁኔታ በሂደት ቤተ ክርስቲያኗን የባለቤትነት መብቷንና መለያ ምልክቶቿን ሊያሳጣት ይችላል የሚል ስጋት አለኝ፡፡ ጉዳዩ በዚህ ከቀጠለ በእምነት ላይም ግራ መጋባት ሊፈጥር ይችላል፡፡ በመሰረቱ የሌላውን ንብረት ሳያስፈቅዱ መውሰድ መጠቀም ከሥርቆት ተለይቶ አይታይም፡፡

ሐመር- ችግሮች አሉ ካልን መወሰድ ያለባቸው መፍት ሔዎች ምንድናቸው?

መንግሥቱ ጎበዜ፡- የኢ/አ/ተ/ቤ/ክርስቲያን የቅርሶች ባለቤነት መብቷን ለማስከበር በርካታ ሥራዎችን መሥራት ይጠበቅባታል፡፡ ከሁሉ በፊት ግን ቅርሶቿ አሁን ያሉበትን አጠቃላይ ሁኔታ ማጥናትና ለአያያዝ፣ ለቆጠራ፣ ለዕይታ፣ በሚመች መንገድ መገኘታቸውን መለየት ይኖርባታል፡፡ ቅርሶችን በዓይነት፣ በቦታ፣ በይዘት፣ በዕድሜና በመሳሰሉት መስፈርቶች መዝግቦ በመያዝ ለቆጠራ፣ ለቁጥጥርና ለአስተዳደር ሥራ አመቺ እንዲሆኑ ማድረግ ይቻላል፡፡ ቅርሶችን በአግባቡ መዝግቦ የትና በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ ለይቶ ማወቅም ከዝርፊያ፣ ከአያያዝ ጉድለቶች የሚፈጠሩ ችግሮችን ለመቅረፍ ትልቅ አስተዋጽኦ ይኖረዋል፡፡ ከዚህ ሌላ ዘመናዊ የምስል ወድምፅ ክምችት ሥርዓት እና አገልግሎት መዘርጋት ቅርሶቹ ተለይተው እንዲታወቁ፣ ሕጋዊ ጥበቃ እንዲደረግላቸውና ተገቢውን እንክብካቤ ለማግኘት ይረዳል፡፡ ከዚህ ሌላ ቤተ ክርስቲያኗ በቅርሶች ጥበቃ ዙሪያ ጠንካራ መመሪያዎችን፣ ደንቦችንና ፖሊሲዎችን ቀርጻና ተቋማትን አጠናክራ መንቀሳቀስ ይጠበቅበታል፡፡

እነዚህና የመሳሰሉ ተግባራት ከተከናወኑ በኋላ የቅርሶቿን የባለቤትነትና የይዞታ መብት ለማስከበር አስፈላጊ የሆነውን ሕጋዊ ክትትልና እርምጃ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ተባብራ ማስኬድ ትችላለች የሚል እምነት አለኝ፡፡

 

  • ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት 21ኛ ዓመት ቁጥር 8 2006 ዓ.ም.

 

ሕገ ወጥ ልመናን የሚያስፋፉ ግለሰቦች ላይ እርምጃ እንዲወሰድባቸው ተጠቆመ፡፡

ጥር 26 ቀን 2006 ዓ.ም.

በቅርቡ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት በቤተ ክርስቲያን ዕድሳት ስም ፈቃድ ሳይሰጣቸው በየዐደባባዩና በአልባሌ ቦታዎች ልመናን የሚያስፋፉ ሕገ ወጥ ግለሰቦች ላይ እርምጃ እንዲወሰድባቸው ተጠቆመ፡፡

የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ እንዳስታወቁት በየአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ላይ ለሚደርሰው ተፈጥሮአዊና ሰው ሠራሽ አደጋ እንዲሁም አዲስ ለሚታነፁ አብያተ ክርስቲያናት ለማሠሪያ የሚሆን ገንዘብ ምእመናንንና በጐ አድራጊዎችን ለመጠየቅ የሚያስችል ፳፬ አንቀጾች ያሉት ደንብና መመሪያ ተዘጋጅቷል፡፡ ደንቡና መመሪያው ለሁለት ዓመት የሚያገለግል ሲሆን ከሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ጥያቄ ሲቀርብ ፈቃድ ይሰጣል፡፡

ይሁንና ይኼን አጋጣሚ በመጠቀም ሕገ ወጥ ልመና የሚፈጽሙ ግለሰቦች ከተሰጠው ፈቃድ ውጪ ጊዜ ያለፈበትን የፈቃድ ደብዳቤ በመያዝ በየዐደባባዩ ሥዕለ አድኅኖ በማስቀመጥና ምንጣፍ በማንጠፍ ይለምናሉ፡፡ ድምፅ ማጉያ በመጠቀም በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም መጻሕፍት፣ ካሴትና ሲዲ ግዙ በማለት ምእመናንን ያውካሉ፡፡ እነዚህን ግለሰቦች ሕግ አስከባሪው አካል እርምጃ እንዲወሰድባቸው ለሁሉም ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ፖሊስ ኮሚሽን በቁጥር 435/11686/06 በቀን 08/02/2006 ዓ.ም የተጻፈ ደብዳቤ ተላልፏል፡፡

የዕቅድና ልማት መምሪያ ሓላፊ የሆኑት አቶ እስክንድር ገ/ክርስቶስ በቁጥር 10273/11686/2005 በቀን 24/11/2005 ለፌደራል ፖሊስ ከሚሽንና ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን በጻፉት ደብዳቤ ያለ አግባብ በየመንገዱ የሚለምኑ አካላት ሕዝበ ክርስቲያኑን ግራ ከማጋባት በተጨማሪ ለጸጥታ አስከባሪዎች ችግር እየፈጠሩ መሆናቸው ከፖሊስና ከጸጥታ አካላት እየተገለጸ መሆኑን አስታውሰዋል፡፡

የከተማውን ሕዝብ በድምፅ ማጉያ እየረበሹ በቤተ ክርስቲያን ስም የሚነግዱትን ሕገ ወጦች እርምጃ እንዲወሰድባቸው እንጠይቃለን በማለት አቶ እስክንድር ተናግረዋል፡፡

ለቤተ ክርስቲያን ግንባታ ፈቃድ የሚሰጠው ለሁለት ዓመት ሲሆን የሚሰበሰበው ገንዘብ ሕጋዊ በሆነ ደረሰኝ በሞዴል 30 ገቢ ይደረጋል፡፡ የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤትም በተሰጠው ፈቃድ መሠረት የተሰበሰበው ገንዘብ በትክክል አገልግሎት ላይ መዋሉን እየተቆጣጠረ እንዲሠራና የቤተ ክርስቲያኑ ሥራ ሲጠናቀቅ ለዕቅድና ልማት መምሪያው እንደሚያሳውቅ ሕገ ደንቡ እንደሚገልጽ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በጎዳና ላይ ልመና እንዲካሔድ ቤተ ክርስቲያን ፈቃድ አትሰጥም፤ ሕጋዊ ባልሆነ መንገድ ሥዕለ ቅዱሳንና ልዩ ልዩ ንዋያተ ቅድሳት በመያዝ በየጐዳናው የሚለምኑ ወገ ኖችን በሕግ ለመጠየቅ ከፌደራልና ከክልል ፖሊስ ጋር እየሠራን እንገኛለን ሲሉ አቶ እስክንድር አመልክተዋል፡፡

በልመና ላይ የተሠማሩት ካህናት ሳይሆኑ ካህን መስለው የሚንቀሳቀሱ ግለሰቦች መሆናቸውን የጠቀሱት አቶ እስክንድር ወደፊት የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎችን ለመሥራት መታቀዱን ገልጠዋል፡፡

 

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 21ኛ ዓመት ቁጥር 8 2006 ዓ.ም.