ዘመነ አስተርእዮ

 ጥር 21 ቀን 2006 ዓ.ም.

 

ር/ደብር ብርሃኑ አካል

አስተርእዮ ቃሉ የግእዝ ቃል ሲሆን መታየት መገለጥ ማለት ነው፡፡ ገሐድ የሚለው ቃልም በጾምነቱ ሌላ ትንታኔ ሲኖረው ትርጉሙ ያው መገለጥ ማለት ነው፡፡ በግሪክ ኤጲፋኒ ይሉታል፡፡ የኛም ሊቃውንት ቀጥታ በመውሰድ ኤጲፋኒያ እያሉ በዜማ መጻሕፍቶቻቸው ይጠሩታል፡፡ ትርጉሙም ከላይ ከጠቀስናቸው ጋር አንድ ነው፡፡

አስተርአየ የተባለው ግሥ ራሱን ችሎ ሳይለወጥ በአምስቱ አዕማድ የሚፈታ ብቸኛ ግሥ ነው፡፡ ይህም ማለት፡- አስተርአየ፤ ታየ፤ ተያየ፤ አሳየ፤ አስተያየ፤ አየ ተብሎ ይፈታል ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ዘመነ አስተርእዮ ሲያጥር ከጥር 11 ቀን እስከ ጥር 30 ቀን ይሆናል፡፡ በዚህም መሠረት 20 ቀናት ይሆናሉ፡፡ ሲረዝም ደግሞ ከጥር 11 ቀን እስከ መጋቢት 3 ቀን ይሆናል፡፡ ይህም 53 ቀናት ይሆናሉ ማለት ነው፡፡

 

ጌታን ለሐዋርያት ህፅበተ እግር ያደረገበት ቀንም ከጸሎተ ሐሙስ እስከ ጰራቅሊጦስ ቢቆጠር 53 ቀናት ስለሚሆኑ የእነዚህ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ዮሐንስ በጥምቀት ዕለት ለልዕልና /ጌታ ሰውን ምን ያህል እንዳከበረው/ ለማሳየት እጁን ከጌታ ራስ በላይ ከፍ እንዳደረገ ጌታም ለትህትና እጁን ከሐዋርያት እግር በታች ዝቅ አድርጎ እግራቸውን አጥቧቸዋልና ነው፡፡ ጥምቀት የህጽበት አምሳል ሲሆን፤ /ህጽበት/ መታጠብ በንባብ አንድ ሆኖ ሁለት ምሥጢራት አሉት፡፡

አንደኛ፤- ምእመናን የእንግዳ እግር እንዲያጥቡ ትምህርት ማስተማሩ ሲሆን፤ ሁለተኛው ለሐዋርያት ጥምቀት ነው፡፡

በጸሎተ ሐሙስ ቢጠመቁም መንፈስ ቅዱስ የተቀበሉት የጰራቅሊጦስ ነውና ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ፤ ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሳርያን ስለ ቅዱሳን ሐዋርያት ጥምቀት እንደጠየቀውና ጥምቀታቸው ህጽበተ እግር መሆኑን እንደመለሰለት፡፡

 

በሌላ በኩል ከዘመነ ልደት እስከ ጥምቀት ተወልደ፤ ተሰገወ /ሰው ሆነ/ ይባላል እንጂ አስተርአየ አይባልም፡፡ ከጥምቀት በኋላ ግን አብሮ ተባብሮ ተጠምቀ፤ ተወለደ፤ ተሰገወ አስተርአየ ይባላል፡፡ ከጥምቀት በፊት አስተርእዮ ለመባሉ በሦስት ነገሮች ነው፡፡

 

አንደኛ፡- የማይታየው ረቂቅ አምላክ በበረት ተወልዶ፤ በጨርቅ ተጠቅልሎ ቢታይና እንደ ሕፃን ሲያለቅስ ቢሰማም ሰው ሁሉ ሠላሳ ዓመት ሲሞላው ሙሉ ሰው ይሆናል እንደሚባለው፤ አምላክ ነኝ ብሎ በአንድ ቀን ሳያድግ በጥቂቱ ማደጉንና ስደት እንደ ውርደት ሆኖ እንዳይቆጠር ለሰዎች ጀምሮ ለመስጠት፤ ሄሮድስም ሊገድለው ይፈልገው ስለነበር የሚሰደድበት እንጂ የሚታይበት ስላልነበረ ነው፡፡

 

ሁለተኛ፡- ሰው በተፈጥሮም ሆነ በትምህርት አዋቂ ቢሆን ለሚመለከተው ሥራና ደረጃ እስከ ተወሰነ ጊዜ ይህ ሕፃን ለእንዲህ ያለ ማዕረግ ይሆናል አይባልም፡፡ ተንከባክባችሁ አሳድጉት ይባላል እንጂ፤ አዋቂ ነው አይባልም፡፡ ያውቃል ተብሎም ለትልቅ ደረጃ አይበቃም፡፡ በየትኛውም ሓላፊነት ላይ አይሰጥም ራሱን በመግዛት ይጠበቃል እንጂ፡፡ እንዲሁም ጌታ የመንፈሳዊ እና የሥጋዊ ባለሥልጣን ቢሆንም ፍፁም ሰው ሆኗልና የሰውን ሥርዓት ከኃጢአት በቀር ለመፈጸም በበሕቀ ልሕቀ ይላል፡፡ አምላክ ነኝና ሁሉን በዕለቱ ልፈጽም ሳይል በየጥቂቱ ማደጉን እናያለን፡፡ በዚህም የተነሣ ሰው ሁሉ 30 ዓመት ሲሆነው ሕግጋትን እንዲወክል እንዲወስን እስከ 30 ዓመት መታገሡ ስለዚሁ ነው፡፡ ከሠላሳ ዓመት በኋላ ግን ሰው ቢመቸው ይወፍራል፤ ቢከፋው ይከሳል እንጂ ቁመት አይጨምርም አይቀንስም፡፡ ስለዚህ ጌታ ሙሉ ሰው የ30 ዓመት አዕምሮው የተስተካከለለት ሰው /ጎልማሳ ሆኖ በመታየቱ ዘመነ አስተርእዮ ተብሏል፡፡

 

ሦስተኛው፤- በ30 ዓመት እሱ ሊጠመቅበት ሳይሆን የመጀመሪያ መንፈሳዊ ሕግና ሥርዓት መሠረት የሆኑ ጥምቀትንና ጾምን ሰርቶ በመሳየትና መመሪያ አድርጎ በመስጠት አምስት ገበያ ያህል ሰው የቃሉን ትምህርት ለመስማት፤ የእጁን ተአምራት ለማየት፤ እሱ ሙሉ ሰው ሆኖ ተገልጾ ትምህርት፤ ተአምራት የሚያደርግበት ሥራዬ ብሎ የመጣበት መንፈሳዊ ሕግና ሥርዓት የተፈጸመበት ዘመን ነው፡፡

 

የታየውም ብቻ አይደለም፤ አብ ይህ የምወደው ልጄ ነው፤ ሲል መንፈስ ቅዱስም በእርግብ አምሳል ረቂቁ የታየበት የሥላሴ አንድነትና ሦስትነት ምሥጢር የተገለጠበት ስለሆነ ዘመነ አስተርእዮ ተብሏል፡፡

 

በዚህ ምክንያትም ሌሎች በዓሎችም ይጠሩበታል፡፡ ለምሳሌ ድንግል ማርያም ጥር 21 ቀን ነፍሷ ከሥጋዋ ተለይቶ በደመና ተነጥቃ ወደ ገነት በመግባት ለጻድቃን ሰዎችና ለመላእክት በሰማይና በምድር የተሰጣት ጸጋና ክብር የተገለጸበት ዕለት ስለሆነ በዓሉ አስተርእዮ ማርያም ይባላል፡፡ የኢትዮጵያ ሊቃውንት በዚህ ቃል ሐሳባቸውን ያስተባብራሉ፡፡ ቅዱስ ያሬድ አምላክ በሥጋ ከድንግል መወለዱን በዚህ አካለ መጠን ለዓለም መገለጡን አስተርእዮ ብሎ ሲናገር፤ አባ ጽጌ ብርሃን ደግሞ በማኅሌተ ጽጌ “የትንቢት አበባ እግዚአብሔር እኛን ሥጋ የሆነውን የአንቺን ሥጋ ለብሶ በምድር እንደተገለጠ ለእኛም እንዲታወቅ ድንግል ሆይ የወገናችን መመኪያ ዛሬ ለእናታችን ለማርያም በሰማይ ፍጹም በደስታ መገለጥ ሆነ እያልን እናመሰግናለን” ብሏል፡፡ ዳዊትም እንዲህ አለ “በከመ ሰማዕና ከማሁ ርኢነ” መዝ. 47፡6 ፡፡ በነቢያት ይወለዳል ሲባል የሰማነው በበረት ተጥሎ፤ በጨርቅ ተጠቅልሎ በግዕዘ ሕፃናት ሲያለቅስ ሰማነው እንዲሁም በዮርዳኖስ ሲጠመቅ አየነው፡፡