limena

የጎዳና ላይ ልመና የቤተ ክርስቲያን ገጽታ የጠቆረበት ሕገ ወጥ ተግባር

 

ዲ/ን ማለደ ዋስይሁን

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የነበራትን መተዳደሪያ በደርግ ዘመን ሙሉ ለሙሉ ማለት በሚያስችል ደረጃ ማጣቷ ይታወቃል፡፡ ይህ በመሆኑ ለብዙ ደካማ ገጽታዎች መፈጠር ምክንያት ሆኗል፡፡ አጥቢያዎች ለካህናት ደሞዝ፣ ለንዋየ limenaቅድሳት መግዣ፣ በአጠቃላይ ለአገልግሎቱ መስፋትና ማደግ የሚያስፈልገውን መተዳደሪያ ገንዘብ፣ ቁስ፣ ጉልበት ለማግኘት ከምእመናን ገንዘብ መለመን ግድ ሆኖባቸው ቆይቷል፡፡

 

ቤተክርስቲያን አስቀድሞም መተዳደሪያዋን የምታገኘው ቤታቸው ከሆነችላቸው ከተገልጋዮቹ ካህናትና ምእመናን ነው፡፡ አማኞች ዐሥራት በኩራት ማውጣት ሃይማኖታዊ ግዴታቸው ነው፡፡ ይሁን እንጂ በዚያ ደረጃ የምእመናን ተሳትፎ ባልተሟላበት ሁኔታ አገልግሎቱ እንዲቀጥል የሚፈልጉ የቤተክርስቲያን ቤተሰቦች ገንዘብ በመስጠት በመሰብሰብ የአጥቢያቸውን አገልግሎት የሰመረ ያደርጋሉ፡፡

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎቷን በማስፋት፣ በማሳደግ ረገድ ነገሥታቱን ጨምሮ በሀገሪቱ ትልቅ ክብርና ስም ከነበራቸው ልጆቿ ጀምሮ የሚበረከትላትን መባዕ ማለትም ገንዘብ፣ መሬት፣ ወርቅ፣ ብር ወዘተ ስትጠቀም ኖራለች፡፡ በኋላ ዘውዳዊ ሥርዓቱ እንዲጠፋ ሲደረግ ቤተክርስቲያን መተዳደሪያዋ ሁሉ በመወረሱ የካህናቱ አገልግሎት ፈተና አጋጥሞታል፡፡ ስለዚህ መውጫ መንገድ ነው የተባለው የሰበካ ጉባኤ አደረጃጀት እንደ አንድ መፍትሔ የደረሰላት ቢሆንም አሁንም ግን በሚፈ ለገው ደረጃ አገልግሎቷን መደገፍ የሚያስችል በቂ ገቢ ባለመኖሩ ችግሩ እንዳለ ነው፡፡

ከዚሁ ጋር ተያይዞ የበለጠ እየተጎዱ ያሉት ደግሞ የገጠር አብያተ ክርስቲ ያናት ናቸው፡፡ ቤተክርስቲያን የምትሰ በስበውን ገንዘብ አሰባሰብና ሥርጭቱ አጠቃቀሙ የገንዘብ አስተዳደር ሥርዓቱ መሻሻል ያለበት ቢሆንም ባለው ደረጃም ቢሆን በችግር ላይ ያሉ አጥቢያዎች መኖራቸው ይታወቃል፡፡ እነዚህ ችግረኛ ገዳማትና አድባራት የሚያስፈልጋቸውን ገቢ ለማግኘት በዓመታዊ በዓላት ከምእመናን የሚያገኙት ገቢ ብቻውን በቂ ባለመሆኑ ልመና ለማድረግ እየተገደዱ ቆይተዋል፡፡ ልመናውንም በተለያዩ አጥቢያዎች በማድረግ የተወሰነ ገቢ አግኝቶ አገልግሎታቸውን ለማስቀጠል እየተንገዳገዱ ነው፡፡

 

ይሔ በእንዲህ እያለ በተቸገሩ አብያተ ክርስቲያናት ስም በጎዳና ላይ ልመና የማድረግ አካሔድ እየሰፋና እያደገ መምጣቱ ይታያል፡፡ ይሔ አካሔድ እጅግ አደገኛና የቤተክርስቲያንንም ገጽታ እየጎዳ ያለ ሕገወጥ አካሔድ ነው፡፡

በቤተክርስቲያን ስም የሚፈጸም የጎዳና ላይ ልመና ገጽታ ሲገመገም አብዛኛው ስምሪት በአዲስ አበባና በሌሎች ዋና ዋና ከተሞች የሚደረግ ነው፡፡ የሚደረጉት የጎዳና ላይ ልመናዎች በዓላት በሆኑ ጊዜያትም ከበዓላትም ውጪ የሚደረጉ ናቸው፡፡ የሚደረጉት ልመናዎች ከአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ውጪ በተገኙ ተገቢ ባልሆኑ ጎዳናዎች ላይ ነው፡፡ የሚደረጉትን የጎዳና ላይ ልመናዎች የሚያከናውኑት ካህናት የሚመመስሉም የማይመስሉም ሰዎች ናቸው፡፡ ልመናዎቹ የሚደረጉት በቡድን ወይም በተናጠል ነው፡፡ የጎዳና ላይ ልመናዎች ሲፈፀሙ ጥላ ተዘርግቶ የቅዱሳን ሥዕላት ተይዘው ነው፡፡ እነዚህ ቅዱሳት ሥዕላት በክብር የተያዙ ያልተያዙም ናቸው፡፡

 

የጎዳና ላይ ልመናዎች ሕገ ወጥነት

የጎዳና ላይ ልመናዎች ሕገ ወጥ የሚሆኑባቸው ብዙ ምክንያቶች አሉ፡፡

1/ የቤተ ክርስቲያኒቱን ፈቃድ ያልያዙ የጎዳና ላይ ለማኞች


በቅዱሳን እና በአብያተክርስቲያናት ስም የሚለምኑ የተወሰኑ ግለሰቦችና ቡድኖች ሁሉም ሕጋዊ የቤተክርስቲያኒቱ ፈቃድ የሌላቸው ናቸው፡፡ እነዚህ ወገኖች ከአጥቢያ ቤተክርስቲያናቸው፣ ከወረዳ ቤተክህነት፣ ከሀገረ ስብከት፣ ከጠቅላይ ቤተክህነት የተጻፈ ምንም የፈቃድ ደብዳቤ ሳይዙ በሕገ ወጥነት በማጭበርበር የሚሰ ለፉም ናቸው፡፡ እነዚህ አካላት የራሳቸውን የግል ወይም የቡድን ጥቅም ለማርካት ወይም የቤተክርስቲያንን ስም ለማጉደፍ በድፍረት የተሰለፉ ናቸው፡፡
እነዚህ ወገኖች ምእመናን የቅዱሳን ስም ሲጠራ ራርተው ይሰጣሉ በሚል እምነት በድፍረት ገንዘባቸውን ለመሰ ብሰብ የሚሹ ናቸው፡፡ በዚህ ምክንያት የትኛውም ሕግ በማይደግፋቸው አግባብ በማን አለብኝነት የዋሕ ወገኖችን እያታ ለሉ ያሉ ናቸው፡፡

2/ የተጭበረበሩ ደብዳቤዎች የያዙ የጎዳና ላይ ልመናዎች

አንዳንዶች ደግሞ ሕጋዊ ለማኝ ለመምሰል ከአጥቢያ የተጻፉ የሚመስሉ ከጠቅላይ ቤተክህነት የተጻፉ በሚመስሉ ደብዳቤዎችን በጎዳና ላይ ደርድረው የሚለምኑ ናቸው፡፡ እነዚህ ደብዳቤዎች ሕጋዊ ማኅተም የሌላቸው ወይም ማኅተምን ቢኖራቸውም በማጭበርበር በማስመሰል የተዘጋጁ ወይም ከዚህ ቀደም ተጽፈው ቀንና ቁጥራቸው ላይ ለውጥ በማድረግ አመሳስለው የሚይዟቸው ናቸው፡፡ በዚህም ምክንያት ሕገ ወጥ ናቸው፡፡

3/ በመመሳጠር የተዘጋጁ ደብዳቤዎችን መጠቀም

በአንዳንድ አጥቢያዎች ያሉ የሰበካ ጉባኤ ሓላፊዎች ወይም ሰነዶችን ሕጋዊ የማድረግ ዕድል ያላቸው ግለሰቦች ከአጠቃላዩ የሰበካ ጉባኤ፣ ከማኅበረ ካህናቱና ከምእመናን ስምምነት ሳይደ ረስባቸው ቤተክርስቲያኑ በጎዳና ላይ እንዲለምኑለት ለተወሰኑ በስም ለተጠቀሱ ግለሰቦች ፈቃድ የሰጠ በማስ መሰል በሚወጡ ደብዳቤዎች የሚፈጸሙ የጎዳና ላይ ልመናዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ደብዳቤዎችን ይዞ አንድ መርማሪ በአጥቢያው ያሉ የሁሉንም የሰበካ ጉባኤ አባላት ወይም የልማት ኮሚቴ ዎች ስምምነት ያገኘ ወይም ያላገኘ ስለመሆኑ ማስረጃ ቢፈልግ በቀላሉ እንዲህ መሰል ደብዳቤዎች የሚወጡበትን የሙስና መንገድ ሊደርስበት ይችላል፡፡

4/ ከያዟቸው ደብዳቤዎች የፈቃድ ሐሳብ በወጣ መልኩ ልመና ማድረግ

ከየትኛውም የቤተክህነት አካል በሕጋ ዊነት የሚወጡ ደብዳቤዎች የቤተ ክርስቲያን አገልግሎትን የሚፈጽሙ ወገኖች የቤተክርስቲያንን ወይም የቅዱሳንን ስም እየጠሩ ሥዕል ይዘው በጎዳና ላይ እንዲለምኑ ፈቃድ አይሰጥም፡፡ በአብዛኞቹ የምእመናን ድጋፍ እንዲጠይቁ ፈቃድ የሚሰጣቸው አገልጋዮች ከአጥቢያ ቤተክርስቲያን ውጪ እንዲህ ባለ ግብር እንዲገኙ አያዝም፡፡ አብዛኞቹ በተለይም ከጠቅላይ ቤተክህነት የተጻፉ ደብዳቤዎችን ስናይ ልመና እንዲፈጸም የሚያዙት ልመናው ከሚደረግበት አጥቢያ ጋር በመነጋገርና በመስማማት በዚያው በአጥቢያው ውስጥ ነው፡፡ ስለዚህ ከአጥቢያ ውጪ የሚለምኑ ወገኖች ከያዙት የፈቃድ ደብዳቤ ሐሳብ ውጪ የሚራመዱ ከሆነ ሕገ ወጥ መሆናቸው አይቀሬ ነው፡፡

5/ ገንዘብ መቀበያ ደረሰኝ የሌላቸው የጎዳና ላይ ለማኞች

በጎዳና ላይ የሚለምኑ ሁሉም ማለት ይቻላል ግለሰቦችና ቡድኖች በየትኛውም መጠን ለሚቀርብላቸው ምጽዋት የሚቀ በሉበት ሕጋዊ ደረሰኝ የላቸውም፡፡ ስለዚህ በአድባራትና በገዳማት የሚለምኑት ወገኖች የሰበሰቡት የገንዘብ መጠን ሊታወቅ አይችልም ማለት ነው፡፡ በእርግጠኝነት መናገር የሚቻለው ግን ቤተክርስቲያን እውነተኛ ፈቃድ ስትሰጥ በሕጋዊ ደረሰኝ እንዲሰበሰብ እንጂ ከዚያ በመለስ ምንም ያህል መጠን ያለው ገንዘብ ከምእመናን ቢሰበሰብ ለተለመነለት አጥቢያ በተሰበሰበው መጠን መድረሱን ወይም አለመድረሱን ከዚያም አልፎ የግለሰቦቹ መጠቀሚያ ሆኖ ቀርቶም እንደሆነ በውል ማወቅ አያስችልም፡፡

የዚህ ችግር መንሥኤ ምንድ ነው?

1/ የቤተክርስቲያን ቁጥጥር ልል መሆን


ቤተክርስቲያናችን የራሷ አካል በሆኑ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ስም የሚፈጸሙ ይሔን መሰል የማጭበርበር ድርጊቶች ለመቆጣጠር የዘረጋችው ጊዜያዊ ወይም ቋሚ አሠራር የለም፡፡ ቢኖርም በንቃት አልተንቀሳቀሰም፡፡ ችግሩን በቀላሉ መቅጨት የሚቻል ቢሆንም እየተባበሰ መሔዱ የአሠራር ድክመቱን ያሳያል፡፡ ቤተክርስቲያን ይሔንን ችግር መቆጣጠር የሚኖርባት ለቤተክርስ ቲያኒቱ ክብር ብቻ ሳይሆን በቤተክር ስቲያን ስም የሕዝብ ገንዘብ በግለሰቦች እየተመዘበረ በመምጣቱም ጭምር ነው፡፡ በሌላም በኩል ክርስቲያኖች ቤተክርስቲያንን ለመደገፍ የሚሔዱ በትን ፈቃድ በየጎዳናው በመጥለፍ በቤተ ክርስቲያን ተገኝተው ጸሎት አድርሰው ተባርከው መባቸውን በሥርዓት አስገ ብተው እንዳይሔዱ የሚያደርግ ልማድ ፈጥሯል፡፡ ቤተክርስቲያን በየጎዳናው ላይ ሁሉ እንዳለች እያሰቡ በኪሳቸው ያለውን ገንዘብ እየሰጡ እንዲያልፉ ሆነዋል፡፡ ስለዚህ የዚህ ሁሉ ተጎጂ ራሷ ቤተ ክርስቲያን መሆኗን አውቆ ልል የሆነውን የቁጥጥር ሥርዓት ጠበቅ ማድረግ፣ ምክር መስጠት፣ ካልሆነም ከሕግ አስከባ ሪዎች ጋር በመተባበርም እርምጃ እንዲወሰድ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡

2/ ሙስና

ቤተክርስቲያን እንዲህ መሰል ጥፋቶች በስሟ የሚበቅሉት የግልጽና ስውር የሙስና አሠራሮች በመኖራቸው ነው፡፡ የጎዳና ላይ ልመናዎች እንዲከናወኑ ሕጋዊ ሽፋን ለመስጠት የተሰለፉ በየደረጃው ያሉ የቤተክርስቲያን አስተዳደር ሹማም ንትም እንዳሉ ይጠረጠራሉ፡፡ ለአንድ ቤተክርስቲያን የሚለመንበት በቂ ምክንያት ሳይኖር ወይም ለአንድ ለተወሰነ ጊዜ ችግር የሆነን ነገር ሁሌ እንዳለ በማስመሰል ፈቃድ በመስጠት እንዲለመን የሚያደርጉ ወገኖች አሉ፡፡ ለዚህም ማሳያ የሚሆነው አንዳንድ አብያተ ክርስቲያናት ሕንፃ ቤተክርስቲያን በማሠራት ስም ፕሮጀክቱን በማራዘም ለረጅም ጊዜ እንዲለመንበት በማድረግ ወይም ካለቀም በኋላ ያለ በማስመሰል ልመናዎች እንዲ ቀጥሉ የማድረግ አሠራር አለ፡፡ በዚህም ቢያንስ ዘረፋ ወይም ጥቅማ ጥቅም ለማግኘት የሚሠሩ ወገኖች አሉ፡፡

3/ ሕዝበ ክርስቲያኑ በየዋህነት በማመን መመጽወቱ

ክርስቲያኖች ለለመነ፣ ለጠየቀ መስጠት አግባብና ክርስቲያናዊ ሥነምግባር መሆኑን ስለሚያምኑ በቅዱሳን ስም ተጠርቶ የቅዱሳን ሥዕል ተይዞ ሲለመን ማለፍ ይከብዳቸዋል፡፡ ሌላው ቀርቶ እንዲለምኑበት የተሰጣቸውን የፈቃድ ወረቀት ሐሳብ ወይም የሚቀበሉበትን ሕጋዊ ደረሰኝ የማይጠይቁ ብዙዎች ናቸው፡፡ በሌላም በኩል ለሚሰጡት ሽርፍራፊ ሳንቲም ደረሰኝ መጠየቅ አስፈላጊ ነው ብለው አያምኑም፡፡ ስለዚህም ለእነዚህ ሕገወጥ የጎዳና ላይ ልመናዎች መበራከት የምእመናንንም ድርሻ አለበት፡፡

በእርግጥ አንዳንድ ክርስቲያኖች የተጎዱ አብያተ ክርስቲያናትን ለመርዳት በሚያ ስችል መልክ ተሰባስበው ቀጣይነት ያለው ሕጋዊነትና ሥርዓት ያለው ድጋፍ ችግረኛ ለሆኑ አብያተ ክርስቲ ያናት መስጠት በመጀመራቸው የችግሩ ስፋት የሚቀንስበት ዕድል ሊኖር ይችላል፡፡ የሆነ ሆኖ ግን ምእመናን የጎዳና ላይ ልመና የቤተክርስቲያንን የሃይማኖ ታቸውን ገጽታ የሚያበላሽና ሥርዓት ያጣ ስርቆትንም የሚያባብስ መሆኑን ተረድተው ከዚህ መቆጠብ ካልቻሉ ገንዘባ ቸውን አነሰም በዛም በግልም ይሁን በቡድን ለቤተክርስቲያን በሕጋዊ መንገድ ገቢ ማድረግ እስካልቻሉ ድረስ ችግሩ መቀጠሉ የማይቀር ይሆናል፡፡

limena1የጎዳና ላይ ልመና የሚያስከትለው ችግር

1/ የቤተ ክርስቲያንን ገጽታ ማጥፋቱ

ይህቺ ቅድስትና በቸር ጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ደም የተመሠረተች ቤተክር ስቲያን ክብር ያላት ናት፡፡ ለብዙዎች የእግዚአብሔርን ጸጋ የምታሰጥ ባዕለጸጋ ቤተክርስቲያን ነች፡፡ ‹‹እናንተን እንጂ ያላችሁን አልፈልግም›› እያለች ስታስ ተምር የኖረች ቤተክርስቲያን ነች፡፡ ለምስኪኖች፣ ለተቸገሩ፣ ለደሀ አደጎች ለእጓለ ማውታ ሁሉ የምትደርስ ቤተ ክርስቲያን ነች፡፡ ‹‹ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብፁዕ ነው›› እያለች የምታሰተምር ቤተክርስቲያን ነች፡፡

 

ቤተክርስቲያን ከምእመናን ዐሥራት በኩራታቸውን ተቀብላ የእግዚአብሔርን ገንዘብ የምታስተዳድር እንጂ ዋነኛ ተግባሯ ሙዳየ ምጽዋት መሰብሰብ አይደለም፡፡ ስብከተ ወንጌልን የማንገሥ እንጂ ማዕድን የማገልገል ፍላጎት ያላት አይደለችም፡፡ ማድረግ ሲገባት ደግሞ በሥርዓትና በታማኝነት የምትፈጽምበት አሠራር አላት፡፡

 

የጎዳና ላይ ልመናዎች ግን የቤተ ክርስቲያን መገለጫ ሆነው ተስለዋል፡፡ ማንም ጥላ ይዞ የሚለምን፣ ሥዕል ያንጠለጠለ፣ እጁን የዘረጋ ሁሉ የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን መገለጫ እየሆነ ነው፡፡ ሌሎች ዐበይት ቤተክርስቲያናዊ ተግባራትን ባከናወንን መጠን ክርስቲ ያኖች ሳይጠይቁ የሚያደርጉትን ነገር እኛ ግን ዐበይት ተግባሮቻችንን ቸል ብለን የጎዳና ላይ ልመና ዋነኛ የሥራ ሂደታችን ያደረግነው ያስመስላል፡፡

 

ስለዚህ ነው ቤተክርስቲያናችን የጎዳና ላይ ልመናዎችና መሰል ተገቢ ያልሆኑ ተግባራት ለቤተክርስቲያኒቱ ታሪካዊነት የአርአያነት ሚና የታማኝነት ደረጃ ወዘተን የሚያኮስሱ ይሆናሉ፡፡

2/ የቅዱሳንን ክብር የሚነካ ይሆናል


ቅዱሳንን እግዚአብሔር ያከበራቸው ናቸው፡፡ ሰዎች ክብርን የሚሰጧቸው ወይም የሚቀንሱባቸው አይደሉም፡፡ እነርሱን በማክበር ግን ቤተክርስቲያንና ልጆቿ በረከት ያገኛሉ፤ እግዚአብሔርን ደስ ያሰኛሉ፡፡

ነገር ግን በጎዳና ላይ ልመናዎች የምናየው ነገር የቅዱሳን መላእክትን የቅዱሳን ሰዎችን ስም ጠርተው ሥዕል ይዘው የሚለምኑ ወገኖች በተለያዩ አካሔዶቻቸው ቅዱሳንን ያዋርዳሉ፡፡ በስማቸው ሕገ ወጥ ሥራ የስርቆት ተግባር መፈጸማቸው ጽርፈት ነው፡፡ ንዋየ ቅድሳት ከሥርዓት ውጪ በተያዙ መጠን ይጉላላሉ፡፡ ሥዕሎ ቻቸውን ይዘው አጓጉል ቦታዎች ቆመው መታየታቸው ጽርፈት ነው፡፡ ለቅዱሳት ሥዕላት ክብር በሚነፍግ መልኩ በአያያዝ የተጎዱ በሥርዓት ያልተሠሩ ፀሐይና ዝናብ የተፈራረቀባቸው ሥዕላትን ይዞ መቆም ለሃይማኖት ቤተሰቡም ሆነ ለሚከበሩት ቅዱሳን ክብር አለመስጠት ነው፡፡

3/ የክህነትን ክብር የሚነካ ነው

ብዙ ጊዜ በጎዳና ልመና ላይ የተሰማሩ ግለሰቦችና ቡድኖች ካህናት የሆኑም ያልሆኑም ወገኖች ናቸው፡፡ ነገር ግን አርአያ ክህነትን ተላብሰው ስለሚታዩ ሁልጊዜም በጎዳና ላይ ልመና የሚታዩት ካህናት ናቸው ብሎ ሰዎች እንዲያምኑ እያደረገ ነው፡፡ ካህናት የቤተክርስቲያን መልክና ምልክቶች ናቸው፡፡ በእነርሱ ውስጥ የምትከብረው ወይም ገጽታዋ የሚደበዝዘው የቤተክርስቲያን ነው፡፡ የመላው ካህናት ገጽታ ነው፡፡ ካህናትን ዘወትር የሚሰጡ ሳይሆን የሚቀበሉ፣ የሚመጸውቱ ሳይሆን የሚመጸወቱ አስመስሎ ያቀርባል፡፡ ከዚያም አልፎ በክህነት የሚፈጸመው ዋነኛ ተግባር ልመና እንደሆነ አድርገው በክህነት የሚያምኑም ሆነ የማያምኑ ወገኖች እንዲያስቡ ያደርጋቸዋል፡፡

4/ የሀገርን ገጽታ ይጎዳል


ቤተክርስቲያን በሙዳየ ምጽዋት የምእ መናንን የለጋስነት ስጦታ መሰብሰቧ፣ ዐሥራት በኩራትን መሰብሰቧ በሃይማኖቱ ሕግና ሥርዓት የታወቀ መንፈሳዊ ተግባሯ ነው፡፡ ስለዚህ የትኛውም ተመልካች ቤተክርስቲያን በአጥቢያዋ ካሉ ምእመናን ዐሥራት በኩራት ምጽዋትን ሰበሰበች ብሎ የሚነቅፋት አይኖርም፡፡ ነገር ግን በተገቢው መልኩ በተገቢው ቦታና በሕጋዊ መልክ ካልሆነ ይነቅፋል፡፡

 

የጎዳና ላይ ልመና ግን ከቤተክርስቲያን አልፎ ለሀገርም ገጽታን የሚያጎድፍ በሀገር ውስጥና በውጪ ሀገር ጎብኚዎችም ዘንድ ደስ የማያሰኝ በመሆኑ ለሀገራችን አይጠቅምም፡፡ ሀገር ልመናን በመቀነስ ሥራና ሠራተኛነትን ለማስፋፋት ጥረት ማድረግ የሚገባትም ለሰሚና ተመልካች ሳቢ ሁኔታን ለመፍጠር ነው፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ግን ከአጥቢያ ቤተክር ስቲያን ግቢ ውጪ ወጥቶ ከዕለታዊ ችግራቸው የተነሣ ሕዝብ ባለበት ዐደባባይ ከሚለምኑ ነዳያን ጎን ተሰልፎ ከአማ ኙም ከኢአማኒውም ለቤተክርስቲያን ንዋየ ቅድሳት መግዣ፣ ለሕንፃዋ ማሠሪያ ገንዘብ ለመለመን መሞከር ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለው ነው፡፡

 

5/ የአጥቢያና የሀገረ ስብከቶችን ክብር ይነካል

 

የሚለመንላቸው አጥቢያዎች ስማቸው አለአግባብ በየጎዳናው ለረጅም ጊዜ መነሣቱ ክብር አይሆንላቸውም፡፡ በስማቸው ሕገ ወጥ ተግባር ሲከናወን ሲታይ አጥቢ ያውን ለሚያውቁ ምእመናንና ካህናት የሚያምም ይሆናል፡፡ ለአጥቢያው ብቻ ሳይሆን በዚህ ሀገረ ስብከት በዚህ ወረዳ ለሚገኘው ተብሎ ስለሚለመን ለዚያ ሁሉ ወገን የሚያምም ይሆናል፡፡

6/ ሥራ ፈትነትን ያበረታታል

ቤተክርስቲያን ያላት ትምህርት ‹‹ሊሠራ የማይወድ አይብላ›› የሚል ነው፡፡ ነገር ግን ሕገ ወጥ የጎዳና ላይ ልመናዎች በአቋራጭ መክበርን ያለሥራ ያለድካም መጠቀምን የሚያመጡ ናቸው፡፡ በመሆኑም ጉዳቱ ለዜጎች ሁሉ ነው፡፡ የሚሠራውን ተስፋ የሚያስቆርጥና ተመሳሳይ የአቋራጭ መንገዶችን እየፈለገ ምርታማ ባልሆኑ ሥራዎች በመሰማራት ከዚያም አልፎ በሥራ ፈትነት በሕገ ወጥ ተግባራት ውስጥ እንዲገባ ያበረታታሉ፡፡ የቤተክርስቲያንን አርአ ያነትም ያጎድፋል፡፡

7/ ለቤተ ክርስቲያን ቤተሰቦች ያሳፍራል

ቤተ ክርስቲያንና ቤተሰቦቿ ከሥራ ይልቅ ልመናን የሚመርጡ ስለሚያስ መስል በሌሎች ወገኖች በሚደርስብን ትችት ምእመናን ይሸማቀቃሉ፡፡ ምእመናን የሚፈለገውን ያህል በማይ ወስኑባት በማይመክሩባት ቤተክርስቲያን ውስጥ ይሔ መሆኑ ደግሞ ምእመናንን የሚያስቆጣበት ደረጃ ላይ ያደርሳል፡፡ ካህናት አመኔታ እንዲያጡ በር ይከፍታል፡፡

8/ ምእመናንን ያዘናጋል

ምእመናን ምጽዋትና ዐሥራት በኩራትን ለይተው ማድረግ እንደሚገባቸው በውል ትምህርት በበቂ ባልተሰጠበት ሁኔታ ውስጥ እንዲህ ያሉ ሕገ ወጥ የጎዳና ላይ ልመናዎች ሲበራከቱ የዋህ ምእመናን ቤተክርስቲያንን ያገኙ ስለሚመስላቸው ዐሥራት በኩራታቸውን በአግባቡ ለማውጣት ይቸገራሉ፡፡ በጥቂቱ በመርካት ከአጥቢያ ቤተክርስቲያን በአፍአ ይቀራሉ፡፡ ምጽዋታቸውንም በአግባቡ ሊሰጡ የሚችሉበት ዕድል አይኖራቸውም፡፡

9/ ሌሎች ችግሮች

የጎዳና ላይ ልመናዎች የሚያስከትሉት ሌላው ጉዳት ከሚለምኑት ሰዎች ማንነትና ተግባር ጋር በተያያዘ የሚያስ ከትለው ችግር ነው፡፡ በልመና ላይ የዋሉ ሰዎች የውሏቸው መጨረሻ የት ነው? የት ያመሻሉ? የት ያድራሉ? ከእነማን ጋር ይውላሉ? የሚለው ሌላው አሳሳቢ ነገር ነው፡፡ ያለደረሰኝ በሕገ ወጥ መልክ የተሰበሰበውን ገንዘብ ይዘው በየመጠጥ ቤቶች ተሰይመው የሚያመሹ በርካቶች ናቸው፡፡ ተደራ ጅተው፣ ማደሪያ ተከራይተው በዓላት ባሉበት የአዲስ አበባ ጎዳናዎች ሁሉ ቆመው ውለው ማታ ተሰባስበው ያገኙትን ገንዘብ ተካፍለው የሚበተኑ ቡድኖች አሉ፡፡ የቡድኖቹ አስተባባሪዎችም አሉ፡፡ ያዘጋጁትን የፈቃድ ደብዳቤ የሚመስል ማጭበርበሪያ ይዘው የሚለምኑ ሰዎችን አደራጅተው ደብዳቤውን ፎቶ ኮፒ አድርገው የሚያሰማሩ ከዚያም ከየለማኞቹ የድርሻቸውን ተቀብለው ለቀጣዩ ዙር ልመና ተቀጣጥረው የሚበታተኑ ሁሉ አሉ፡፡ ይህ ሁሉ የሚፈጸመው በቤተክር ስቲያኒቱ ስም መሆኑ ሲታሰብ የሚያሳዝን ነው፡፡

 

ሌላው አሳሳቢው ነገር በየቦታው በሚታዩ ልመናዎች የሚያስተባብሩት ወይም የሚለምኑት ሰዎች ተጠሪነታቸው ለጥቂትና ተመሳሳይ ሰዎች የመሆኑ ነገር ነው፡፡ እነዚህ ግለሰቦች የፈቃድ ደብዳቤ ብለው በሚይዙት ላይ በልዩ ልዩ ሥፍራዎች ያሉ ሰዎች በያዟቸው የፈቃድ ደብዳቤዎች ላይ በአንድም በሌላ መንገድ ተጠቅሰዋል፡፡ እነዚህ ግለሰቦች በተለይም የአዲስ አበባን የጎዳና ላይ ልመናዎች ገዢ ሆነው የተቀመጡ ሰዎች ናቸው፡፡ ምናልባትም ሕጋዊ መልክ እንዲኖራቸው ከቤተክህነቱ አንዳንድ ግለሰቦች ጋር የጥቅም ግንኙነት ያላቸውም ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ስለዚህ የሚለምኑት ከሚያስለምኑ ሕጋዊ ነን ከሚሉ ገዢዎቻቸው ጋር ተቀናጅተው የሚፈጽሙት ጥፋት ነው፡፡

 

ሌላው አሳሳቢው ነገር የሀገሪቱን ሕግ የሚያስከብሩ ደንብ አስከባሪዎችና ፖሊስ ቤተክርስቲያንን እና ክርስቲያኑን ማኅበረሰብ በመፍራት ለመጠየቅ የሚደፍ ሯቸው አለመሆናቸው ነው፡፡ በፊታቸው የሚዘረጓቸውን ማስፈራሪያ ወረቀቶች አይተው ወይም የሚሰጣቸውን መጽዋች ፈርተው ወይም አይመለከተንም በማለት ወዘተ የሕግ አስከባሪዎች ስለሚያልፏቸው ጠያቂ እንደሌላቸው በማሰብ እነዚህ በቤተክርስቲያን ስም በመለመን የብዙዎችን ገንዘብ አለአግባብ እየዘረፉ ይገኛሉ፡፡

መፍትሔ

ቤተክርስቲያን በስሟ የሚፈጸሙ ልመናዎችን ለማስቆም መትጋት ያለባት አሁን ነው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ሙስናን ከቤተክርስቲያን ለማጥፋት እሠራለሁ ብሎ እየተጋ ባለበት በዚህ ዘመን ከእነዚህ ጥቃቅን ቀበሮዎች ጀምሮ ወደ ታላላቆቹ መገስገስ ይገባዋል፡፡ ታላላቆቹ ሙሰኞች በእነዚህ ጥቃቅን መሠረቶች ላይ የቆሙ ናቸው፡፡

 

ቤተክርስቲያን እንዲህ ያሉ ሕገ ወጦችን ማጥፋት የሚገባት የቅድስና ባለቤት በሆነችው ቤተክርስቲያን ስም የሚፈጸም የስርቆት ተግባር ኃጢአት በመሆኑ ነው፡፡ ስለዚህ በልመና ላይ የተሰማሩትን ጨምሮ በዚሁ የጥፋት መንገድ ለመሳተፍ እየተንደረደሩ ያሉትን ለመታደግ ይረዳታል፡፡ በሌላ መልኩ ምእመናን ገንዘባቸውን በቤተክርስቲያን ስም እንዳይዘረፉ ከመጠበቅ አንጻር ነው፡፡ በሌላ መልኩ ደግሞ የቤተክርስቲያንን ገጽታ እንዳይጎድፍ ከመጠበቅ አንጻር ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በቤተክርስቲያኒቱ መሠልጠን ያለበት ሕጋዊ አሠራር ብቻ መሆኑን አስረግጦ ለማስረዳት ለማሳየት ይጠቅማል፡፡

 

ስለዚህም በቅድሚያ በቤተክርስቲያን ስም በጎዳና ላይ መለመን ከብዙ ነገሮች አንጻር ምን ያህል አግባብ ነው የሚለውን በውል በማጤን ግልጽ አቋም መያዝ ከቤተክርስቲያን ይጠበቃል፡፡ ከዚህ አስከትሎም አሁን በጎዳና ላይ እየተፈጸሙ ያሉ ልመናዎችን ሕጋዊነት መመርመር ያስፈልጋል፡፡ ለጎዳና ላይ ልመናዎች ፈቃድ የሚሰጠው ማን ነው? ፈቃዱን ለእነማን ሰጠ? ለምን ዓላማ ሰጠ? ተግባሩ ፈቃድ በተሰጠበት አግባብ ተፈጽሟል? ፈቃዱ እስከ መቼ የሚሠራ ነው? በፈቃዱ የተሰበሰበው ገንዘብ ለታሰበው ዓላማ እየዋለ ነው? በትክክል የፈቃድ ደብዳቤው ወጣ ከተባለበት መዝገብ ቤት ወጥቷል? ወዘተ የሚሉ ጥያቄዎችን አንሥቶ የቤተክርስቲያኒቱ ታማኝ የሕግ አስከባሪ አካላት ከተለያዩ የሚመለከታቸው አካላት ጋር መመርመርና እርምጃ ማስወሰድ አለባቸው፡፡

ከቤተክርስቲያን አስተዳደር ሌላ ግን ከመንግሥት አካላት ጋር ተባብሮ ቢያንስ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶችና ሌሎች ቁጭቱ ያላቸው አገልጋዮችም የእነዚህን የጎዳና ላይ ልመናዎች ለማስቀረትና የቤተክርስቲያናችንን ክብር ማስጠበቅ አለብን፡፡

መሰናክል ያለበትን ገንዘብ የሚሰበስብ ሰው ገንዘብ በመሰብሰቡ ኃጢአት አድርጓልና እንዳይሰበስብ ይገባዋል/ፍት.ነገ. አንቀ.16 ቁ.648/

ዳግመኛም ገንዘብ እያለው ምጽዋት ለሚቀበል ሰው ወዮለት አለ፤ ራሱን መርዳት እየተቻለው ከሌሎች መቀበልን የሚወድ ሰው ወዮለት እንዲህ ያለውን ግን በፍርድ ቀን እግዚአብሔር ይመረምረውል››/ፍት.ነገ.አንቀ.16 ቁ.634/

ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት፤21ኛ ዓመት ቁጥር 7፤ ኅዳር 2006 ዓ.ም.