የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዝርወት

ሐምሌ 3 ቀን 2005 ዓ.ም

በዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ

የዚህ ጽሑፍ ዓላማ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዝርወት /ከኢትዮጵያ ውጭ/ ያደረገችውን ረጅም ሐዋርያዊ ጉዞ በአጭሩ በመዳሰስ፤ ጉዞዋ ዛሬ የደረሰበትን ምዕራፍ መቃኘት ነው፡፡ የዛሬው ከታየ ዘንድ ግን ጽሑፉ በመጠኑም ቢሆን ጥናታዊ መልክ ይኖረው ዘንድ ዛሬ ቤተ ክርስቲያኗ በውጭው ዓለም ለምትሰጠው አገልግሎት እንቅፋት ናቸው ተብለው ሊጠቀሱ ከሚችሉ ችግሮች ዋና ዋና የሚባሉትን በማቅረብ የይሁንታ አሳብ ይሰነዝራል፡፡

ኢትዮጵያ እንደ ሀገር እምነትን በተመለከተ የግንኙነት መስመሯን ወደ ውጭ መዘርጋት የጀመረችው ቅድመ ክርስትና ከ1000 ዓ.ዓ. ገደማ ጀምሮ ነው፡፡ በቃልም በመጣፍም የቆየን የሀገራችን ወፍራም የእምነት ታሪክ እንደሚነግረን ንግሥተ ሳባ በሕገ ልቡና እግዚአብሔርን ሲያመልክ የነበረ ሕዝቧን በመወከል ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዛ ከንጉሡ ከሰሎሞን ጋር በመወያየት እግዚአብሔር ለእሱና ለሕዝቡ የገለጠውን ሕገ ኦሪት ይዛ ወደ አገሯ ተመልሳለች፡፡ ሕዝቧንም በዚሁ የኦሪት ሕግና እምነት እንዲመራ አድርጋለች፡፡ እሷ የጀመረችው ግንኙነትም በኋላ የመንፈሳዊ ጥበብ ፍለጋ ጉዞዋ ሌላ ውጤት በሆነው ልጇ ቀዳማዊ ምንልክና እሱ ባመጣቸው ሌዋውያን ካህናት አማካይነት ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡

ከክርስትና በፊት የነበረውን ድዮስጶራዊ እንቅስቃሴና ግንኙነት በዚሁ እንተወውና የክርስቶስ መወለድና ታላቅ የማዳን ሥራ ለዓለም ከታወጀበት ወዲህ ያለውን ታሪክ እንመልከት፡፡ መግቢያ ይሆነን ዘንድ የዝርወት እንቅስቃሴዋን የምናይላት የኢ.ኦ.ተ.ቤ. እንዴት እንደ ተመሠረተች በሌላ አገላለጥ ክርስትና ወደ ሀገራችን እንዴትና መቼ እንደገባ በአጭሩ እንመልከት፡፡ እኛ ኢትዮጵያውያን ከክርስትና ጋር የተዋወቅንበትን ጊዜ አስመልክቶ ከላይ እንደተጠቀሰው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአበው ያስቆጠረው ሱባኤ ሞልቶ፣ በነቢያት ያስነገረው ትንቢት እውነት ሆኖ በቤተልሔም በተወለደ ጊዜ ይህንን ታላቅ ዜና በጥበብ ተረድተው፣ በኮከብ እየተመሩ ቤተልሔም ደርሰው በመስገድ ለንጉሠ ሰማይ ወምድርነቱ ወርቅ፣ ለክህነቱ ዕጣን፣ አዳምን ለማዳን በመስቀል ላይ ስለሚቀበለው ሕማምና ሞት ከርቤ እጅ መንሻ አቅርበው ወደ ሀገራቸው ከሔዱት ነገሥታት አንዱ ኢትዮጵያዊ ነው የሚል ታሪክ አለ፡፡

በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት አምኖ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስስም ተጠምቆ ክርስትናን በመያዝ ወደ ሀገራችን የገባው የኢትዮጵያ ንግሥት ሕንደኬ በጅሮንድ /የገንዘብ ሹም/ የነበረው ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ነው፡፡ እንደኦሪቱ ሥርዐት ማንኛውም የብሉይ ኪዳንን እምነት የተቀበለ ወንድ የሆነ ሁሉ በዓመት የሚያከብራቸው በዓላት ነበሩ፡፡ እነዚህም በዓላት በዓለ ናዕት /የቂጣ በዓል/፣ በዓለ ሰዊት /የእሸት በዓል/፣ በዓለ መጸለት /የዳስ በዓል/ ይባሉ ነበር፡፡ በዚህም መሠረት በርካታ ኢትዮጵያውያን የእምነታቸው ሥርዐት በሚያዝዘው መሠረት ከበዓለ ፋሲካ ሰባት ሱባኤ በኋላ የሚከበረውን በዓለ ሰዊትን ወደ ኢየሩሳሌም መንፈሳዊ ጉዞ በማድረግ ያከብሩ ነበር፡፡ /ሶፎ. 3፥10/፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ መዝግቦት በምናገኘው ታሪክ መሠረት ሐዋርያት በጌታ ልደት የተበሰረችውን ወንጌል ያለፍርሐትና ያለመሰቀቅ ዓለምን ዞረው ያስተምሩ ዘንድ አጽናኝ የሆነውን መንፈስ ቅዱስን የላከላቸው በ34 ዓ.ም በዓለ ሰዊት በተከበረበት ዕለት ነበር፡፡ /ሐዋ. 3፥10/ በዚህም መሠረት ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ተቀብለው በየሀገሩ ቋንቋ ሲናገሩና እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ በመደነቅ ከሰሙት ምእመናን መካከል ኢትዮጵያውያንም ይገኙበት እንደነበረ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በዓለ ሐምሳን አስመልክቶ በሰጠው ስብከቱ መስክሯል፡፡ /ድርሳን ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ዘበዓለ ሃምሳ/፡፡

በዚሁ በዓል ተሳትፎ የቅዱሳት መጻሕፍትን ምሥጢር እየመረመረ ወደ ሀገሩ በመመለስ ላይ የነበረው ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ ከወንጌላዊው ፊል ጶስ ጋር ተገናኘ፡፡ ፊልጶስም ያነበው የነበ ረውን የትንቢት መጽሐፍ ለክርስቶስ እንደተነገረ አምልቶ አስፍቶ ተረጎመ ለት፡፡ ጃንደረባውም በትምህርቱ አመነ፡፡ ተጠመቀ፡፡ በዚህ ዓይነት ክርስትናን ይዞ ወደ ኢትዮጵያ ገባ፡፡ እሱም በተራው ይኸንኑ የክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት ዜና ለሕዝቡ አሰማ፡፡ /ሐዋ. 8፥26-40/ አውሳብዮስ ዘቂሳርያ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ 2ኛ መጽሐፍ ቀ. 1/፡፡ በዚህ ዓይነት እንደ ሕገ ኦሪቱ ሁሉ በቤተ መንግሥቱ በኩል አድርጎ ወደ ኢትዮጵያ የገባው ክርስትና በዐራተ ኛው መ.ክ.ዘ. ተቋማዊ መልክ ይዞ በሀገር ውስጥና በውጭው ዓለም ኢትዮ ጵያዊ ጉዞውን ጀምሯል፡፡

ከላይ ከቀረበው ታሪክ የምንረ ዳው ሀገራችን ኢትዮጵያ አስቀድሞ ከሕገ ኦሪት ኋላም ከሕገ ወንጌል ጋር የተዋወቀችው በዘረጋችው የውጭ ግንኙነት አማካይነት እንደሆነ ነው፡፡

I. የአገልግሎት ጉዞ ከትላንት እስከ ዛሬ
ቤተ ክርስቲያኗ እንደ መንፈሳዊ ተቋም ከተመሠረተችበት ጊዜ ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ በዝርወት ያደረገችውን እንቅስቃሴ እንደሚከተለው በወፍ በረር በክፍል በክፍል እናየዋለን፡፡

1. በመካከለኛው ምሥራቅ   
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በውጭው ዓለም ካላት ሐዋርያዊ ጉዞ ታሪክ ሰፋ ያለውንና ቀዳሚውን ምዕራፍ የሚወስደው በመካከለኛው ምሥራቅ የጻፈችውና ያጻፈችው ነው፡፡ ይህም ሊሆን የቻለው ኢትዮጵያ ከአካባቢው ሀገራት ጋራ ካላት መልክአ ምድራዊ መቀራረብ እንዲሁም የባሕልና የእምነት መዛመድ የተነሣ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ በዚህ አካባቢ ያደረገችው እንቅስቃሴና አስቀምጣ ያለፈችው የታሪክ አሻራ በወግ አልተጠናም፡፡ የሆነው ሆኖ የሚታወቀውን እንቅስቃሴዋን በሀገራቱ በመከፋፈል ለማየት እንሞክር፡፡

1.1 በኢየሩሳሌም
ኢትዮጵያ እምነትን በሚመለከት ከኢየሩሳሌም ጋር ያላት ግንኙነት ከንግሥተ ሳባ ዘመነ መንግሥት ጀምሮ እንደሚሔድ ተመልክተናል፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ሀገራችን ከእስራኤል ጋር ባላት ቅርርብ መሠረት በተለያዩ ጊዜ ያት ልዩ ልዩ ገዳማትን በማቋቋም ስታገለግልና ስትገለገል ቆይታለች፡፡ በአሁኑ ጊዜ ቤተ ክርስቲያኗ በኢየሩሳሌም የራሷ ሀገረ ስብከት ያላት ሲሆን በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ የበላይ ጠባቂነት የሚተዳደሩ ሰባት ቅዱሳት መካናት አሏት፡፡

1.2 በግብፅ
ቤተ ክርስቲያኗ ከምሥረታዋ ጀምሮ ከአምስቱ አኃት አብያተ ክርስቲያናት አንዷ ከሆነችው የግብፅ ቤተ ክርስቲያን ጋር የጠበቀ ግንኙነት ነበራት፡፡ ለ1600 ዓመታት ያህል ግብፃውያን ሊቃነ ጳጳሳት ወደ ሀገራችን በመምጣት ቤተ ክርስቲያኗን መርተዋል፡፡ የዚያኑ ያህል የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንና አባቶችም ወደ ግብፅ እየሔዱ ሐዋርያዊ አገልግሎት ሰጥተዋል፡፡ ከሐዋርያዊ አገልግሎቷ መካከል ለግብፃውያኑ ስለእምነት ነፍስን አሳልፎ መስጠት /ሰማዕትነት/ ተጠቃሽ ነው፡፡ አባ ሙሴ ጸሊም ወደ ግብፅ በመሔድ ልዩ ልዩ ተጋድሎ ሲፈጽም ቆይቶ መነኮሳትን ለማጥፋትና ገዳማቸውን ለማቃጠል አረማዊ ሠራዊት በመጣ ጊዜ ከግብፃውያኑ ቀድሞ ሰማዕትነት ተቀብሏል፡፡ ይህ አባት ሰማዕትነትን እንዲቀበሉ ያጸናቸው ታላቅ ኢትዮጵያዊ ሐዋርያ እንደሆነ ቅዱሳት መጻሕፍት ምስክርነታቸውን ይሰጣሉ፡፡ የዚህ ሐዋርያ ተግባር ተሰዐቱ ቅዱሳንን ወደ ኢትዮጵያ እንደሳበ በስፋት ተመዝግቦ የሚገኝ ታሪክ ነው፡፡

በ11ኛው መ.ክ.ዘ. በአስቄጥስ በረሃ በሚገኘው ዮሐንስ ሐፂር ገዳም ውስጥ የኢትዮጵያውያን መነኮሳት እንደነበሩ፤ በ1330 በ1330 አቡነ ብንያም 2ኛ የተባሉት የግብፅ ፓትርያርክ የዮሐንስ ሐፂርን ገዳም በጎበኙ ጊዜ ኢትዮጵያውያንና ግብፃውያን መነኮሳት በዝማሬ እንደ ተቀበሏቸው፣ ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በገዳመ አስቄጥስ ጉብኝታቸው ወቅት በገዳመ ዮሐንስ ሐፂር ቆይታ ማድረጋቸው፣ የኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ሥዕል በ1517 ዓ.ም በአቡነ መቃርዮስ ገዳም ለጎብኝዎች ማረፊያ በተሠራው ቤተ ክርስቲያን ግድግዳ ላይ ተሰቅሎ መገኘቱ፤ እንዲሁም በግብፅ ውስጥ ዴር አል ሱርያን ተብሎ በሚታወቀው በሶርያውያን ገዳም ኢትዮጵያውያን መነኮሳት ይኖሩ እንደ ነበርና አንድ ትልቅ ቤተ መጻሕፍት እንዳቋቋሙ መዛግብት ያስረዳሉ፡፡ በደቡብ ግብፅ በሚገኘው የቁስቋም ገዳም ከ14ኛው እስከ 17ኛው መ.ክ.ዘ. ድረስ ኢትዮጵያውያን የራሳቸው ገዳም ነበራቸው፡፡ በዚህ ዘመን የተጋድሎን ሕይወት ለግብፃውያኑ ካስተማሩት ኢትዮጵያ ውያን አበው መካከል አቡነ አብደል ጣሉት አል ሐበሽና አቡነ አብደል መሢሕ /ገብረ ክርስቶስ/ በመባል የሚታወቁት ሁለት አበው ተጠቃሽ ናቸው፡፡

በአሁኑ ወቅት ከ1985 ዓ.ም ጀምሮ ብዙ ኢትዮጵያውያን ወደ ግብፅ በስደት በመግባታቸው በግብፅ የአባስያ ሰንበት ት/ቤት አቋቁመው አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡

1.3 በሀገረ ናግራን
በዛሬዋ የመን ደቡብ ዓረቢያ ይገኝ የነበረ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሀገረ ስብከት ሲሆን በዚህ ቦታ ቤተ ክርስቲያን ለ300 ዓመታት አገልግላለች፡፡ በዚህ አካባቢ ጻድቁ ዐፄ ካሌብ በአይሁድና አረማውያን እንግልት የደረሰባቸውን ክርስቲያኖች በማዳን ታላቅ ተጋድሎ ከመሥራታቸውም ባሻገር አብያተ ክርስቲያናትን አሳንፀው ቤተ ክርስቲያኗ የተገፉትን በመጠበቅ የተበተኑትን በመሰብሰብ በኩል ሰፊ አገልግሎት እንድትሰጥ አድርገው ተመልሰዋል፡፡  

1.4 በሶርያ
በዚህ አካባቢ ቤተ ክርስቲያናችን የሰጠችው ሰፊ አገልግሎት በወግ ስላልተጠና ሰፊ ሐተታ ማቅረብ ባይቻልም ዛሬም ድረስ ሙሴ አል ሐበሻ በመባል የሚታወቀው ገዳምና የዐፄ ገብረ መስቀል ልጅ አባ ሙሴ እንደ መሠረተው የሚነገረው ገዳም መገኘቱ ቤተ ክርስቲያናችን በአካባቢው ያላትን ታሪካዊነትና ጥንታዊነት ይመሰክራል፡፡  

1.5 አርመን
ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ ኤዎስ ጣቴዎስ፣ አባ ባኪሞስ፣ አባ መርቆ ሬዎስና አባ ገብረ ኢየሱስ የተባሉ ደቀ መዛሙርታቸውን አስከትለው ግብፅ ወርደው የግብፁን ፓትርያርክ አቡነ ብንያምን አነጋግረው ወደ ኢየሩሳሌም ከሔዱ በኋላ በአርመን በተለይም ዛሬ ቱርኮች በያዟት ሲሲሊያ በተባለች ቦታ ለ14 ዓመታት ሐዋርያዊ አገልግሎት ሰጥተዋል፡፡   

1.6.  በአሁኑ ጊዜ በመካከለኛው ምሥራቅ
ቤተ ክርስቲያናችን ጥንት ቀይ ባሕርን ተሻግራ በመካከለኛው ምሥራቅ የሰጠችውን አገልግሎት በዚህ ዓይነት ካየን ዘንድ በአሁኑ ወቅት በየመን፣ በሰንዓ፣ በዓረብ ኢምሬቶች፣ በሊባኖስ አብያተ ክርስቲያናት መንፈሳዊ አገልግሎት ለመስጠት ተቋቁመዋል፡፡ በዓረብ ኢምሬቶች ውስጥ በሻርጂያ፣ ዱባይ፣ አቡዳቢ እና አል ዓይን ከተሞች አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ለመሥራት እንቅስቃሴው ተጀምሯል፡፡  

 

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት ቁጥር 19 ከሰኔ 1-15 ቀን 2005 ዓ.ም.

ሰዋሰወ ግእዝ ክፍል አራት

ሐምሌ 3 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ት ኑኀሚን ዋቅጅራ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

 

  •  ፊደል ብሂል – ርዕሰ መጻሕፍት -የመጻሕፍት (የጽሑፍ) መጀመሪያ
  • ፊደል ብሂል – ነቅዓ ጥበብ – የጥበብ ምንጭ /የእውቀት መፍለቂያ/
  • ፊደል ብሂል – መጽሔተ አእምሮ – የአእምሮ መስታወት
  • ፊደል ብሂል – ጸያሔ ፍኖት – መንገድ ጠራጊ /በር ከፋች/
  • ፊደል ብሂል – መራሔ እውራን ውእቱ – ፊደል ሰዎችን ካለአዋቂነት /ከድንቁርና እውርነት አውጠቶ ወደ ብርሃን የሚመራ ነው፡፡   

ባለፈው ሳምንት አምዳችን ስለ ግእዝ ፊደላትና ስለ ዝርዋን የግእዝ ፊደላት የአዘራዘር ሥልትና የፊደላት ትርጉም ተመልክተናል፡፡ በዛሬው አምዳችን ደግሞ ስለ አማርኛ ፊደላትና የአማርኛ ዝርዋን ፊደላትን እንመለከታለን፡፡

የአማርኛ ፊደላት የምንላቸው በቁጥር ፯/ሰባት/ ናቸው፡፡ የአማርኛ ፊደላት ከጊዜ በኋላ በዋንኞቹ የግእዝ ፊደላት ላይ የተወሰነ ቅጥያ በማድረግ የተመሠረቱ ፊደላት ናቸው፡፡ የአማርኛ ፊደላት የአዘራዘር ሥልት እንደ መነሻዎቹ የግእዝ ፊደላት ሲሆን በግእዝ በካዕብ በሣልስ በራብዕ በኀምስ፣ በሳድስና በሳብዕ የአዘራዘር ሥልት ይዘረዘራሉ፡፡ የአማርኛ ፊደላት የአማርኛ ፊደል የተባሉበት ዋናው ምክንያት በግእዝ ቋንቋ በሚዘረዘሩ ግሦችና የፊደላት ትርጉም አለመጠቀሳቸውና አብዛኛውን ጊዜ በግእዝ ቋንቋ በሚጻፉ ጽሑፎችና ሥነ ጽሑፍ ላይ አለመጠቀሳቸውም ነው፡፡ ለአማርኛ ፊደላት መነሻ የሆኑትን የግእዝ ፊደላትና የአማርኛ ፊደላትን ከነአዘራዘራቸው በቅደም ተከተል ከዚህ በመቀጠል እንመለከታለን፡፡

ከዚህ የምንረዳው በፊደል ገበታ ላይ የአማርኛ ፊደላት ተብለው ከሚጠሩት ፊደላት መካከል እነዚህ ፯/ሰባት/ ፊደላት ብቻ ሌሎቹ የግእዝ ፊደላት መሆናቸው ነው፡፡

መነሻ የግእዝ ፊደላት

ግእዝ

ካዕብ

ሣልስ

ራብዕ

ኀምስ

ሳድስ

ሳብዕ

       ሰ

 

 

 

 

 

 

        ተ

 

 

 

 

 

 

        ነ

 

 

 

 

 

 

       ከ

 

 

 

 

 

 

        ዘ

 

 

 

 

 

 

        ደ

 

 

 

 

 

 

        ጠ

 

 

 

 

 

 

 

ከዚህ በመቀጠል ደግሞ የአማርኛ ፊደል ዲያሎችን /ዝርዋን የአማርኛ/ ፊደላትን እንመለከታለን፡፡

ዝርዋን የአማርኛ ፊደላት
ዝርዋን ማለት ብትን ሕግንና ቅደም ተከተልን ያልጠበቀ ማለት ነው፡፡ ዝርዋን የአማርኛ ፊደላት የምንላቸው በግእዝና በአማርኛ ፊደላት ላይ በተለየ መልኩ በራብዑ /በአራተኛው/ ፊደል ዝርዝር ላይ በስተመጨረሻ ወይም ከላይ ቅጥያ በማድረግ የተፈጠረ ፊደልና በአንድ ነጠላ ዝርዝር ብቻ የሚገለጽ በአማርኛ ጽሑፍ ላይ ብቻ የሚገኝ የፊደል ዝርዝር ነው፡፡ ዝርዋን የአማርኛ ፊደላት አብዛኛውን ጊዜ የሚያገለግሉት በአንስታይ /በሴት/ ጾታ ማለትም በሩቅ ድርጊት አመልካች በነጠላ የሴት ጾተ የሚገለጸውን ቃል የእራስነትዋን ለመግለጽ የምንጠቀምበትን ቃል ሁለት ተከታታይ ሳድስና ራብዕ ፊደላትን በመዋጥ በአንድ ፊደል በዝርው የአማርኛ ፊደል በመተካት የፊደላትን ቁጥር በመቀነስ ያገለግላል፡፡

ዝርዋን የአማርኛ ፊደላት የሚባሉት
           ሏ፣ ሟ፣ ሿ፣ ሯ፣ ቧ፣ ቷ፣ ዟ፣ ዧ፣……. ናቸው፡፡

ምሳሌ፡- ልብዋ …. ልቧ፣ ቤተሰብዋ…..ቤተሰቧ
           እርስዋ… እርሷ፣ እጅዋ….. እጇ ወዘተ…….

ለዛሬ ያለንን አምድ በዚህ እናበቃለን በቀጣይ ሳምንት የግእዝ አኀዝ ቁጥሮችን የአጻጻፍና የአነባበብ ሥልት እንመለከታለን እስከዚያው ቸር ይግጠመን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

gebi 01

የአዲስ አበባ ማእከል የግቢ ጉባዔያት ተማሪዎችን አስመረቀ

ሐምሌ 1 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል የግቢ ጉባዔያት ማስተባበሪያ ክፍል፤ የቅዱስ ማርቆስ አካባቢ ማስተባበሪያ፤ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን በቅድስትgebi 01 ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ አዳራሽ ሰኔ 30 ቀን 2005 በድምቀት አስመረቀ፡፡ ተማሪዎቹ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ /ከስድስት ኪሎ፤ ከአምስት ኪሎ ቴክኖሎጂ ፋኩልቲ፤ ከአራት ኪሎ የተፈጥሮ ሳይንስና ከቅዱስ ጳውሎስ/ በተለያዩ የትምህርት ዘርፎች በድኅረ ምረቃና በመጀመሪያ ዲግሪ የተመረቁ ሲሆኑ በግቢ ቆይታቸው መንፈሳዊ ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የነበሩ አንድ ሺህ የሚደርሱ ተማሪዎች ናቸው፡፡ 

ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የኢሉባቦርና ጋምቤላ አኅጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመርሐ ግብሩ ላይ በመገኘት ባስተላለፉት ቃለ ምእዳንና ቡራኬ “ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያትን ካስተማራቸውgebi 02 በኋላ በሚሔዱበት ሁሉ አልተለያቸውም፡፡ እሱን መርህ አድርገው በዓለም ሁሉ ተበትነው ወንጌልን አስተማሩ፡፡ እናንተም የእምነትን መሣሪያ ይዛችኋል፤ በሥራችሁ ሁሉ እግዚአብሔር ይከተላችኋል፡፡ እናንተ ቀናዎች ከሆናችሁ ከሚመጣባችሁ ክፉ ነገር ይጠብቀችኋል፡፡ በቀኝ እጃችሁ እምነታችሁን፤ በግራ እጃችሁ ከዩኒቨርስቲ የቀሰማችሁትን እውቀት ይዛችሁ ተሰማሩ፡፡ ቤተ ክርስቲያንንም አገልግሉ” በማለት የአደራ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ በበኩላቸው ለተመራቂ ተማሪዎች የእንኳን ደስ ያላችሁ መልእክት ያሰተላለፉ ሲሆን  “መማር ለማወቅ ነው፤ ማወቅ ለመሥራት፤ መሥራት ደግሞ ለውጤት ነው፡፡ በዚህ ሂደት የሰው ልጅ ባሕርይው እንደተጠበቀ ሆኖ ብዙ ለውጦችን ያሳያል፡፡ እነዚህን ለውጦች በአግባቡ ተጠቅሞ ወደ ውጤት ለመድረስ በተለይም በመንፈሳዊው ትምህርት ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን የመጽሐፍ ቅዱስን ቃል ከተማሩ ወገኖች ብዙ ይጠበቃል፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን በተማሩ ሰዎች ሊሠሩ የሚገባቸው በርካታ ተግባራት አሉ፡፡ እነዚህን ተግባራት ከአጥቢያ ጀምረን እስከ ላይ ድረስ ቀረብ ብለን በማየት፤ እንደየአቅማችንና እንደ ሥራው ሁኔታ ሠርተን ውጤት ልናመጣ ይገባል፡፡ ይህንንም መሠረት በማድረግ በምትሠማሩበት የሥራ ቦታ በግቢ ውስጥ በጥቂቱ የጀመራችሁትን መንፈሳዊ ጉዞ አብዝታችሁ እንድትቀጥሉ መንፈሳዊ ጥሪያችንን እናቀርባለን ” ብለዋል፡፡gebi 03

“ህያዋን ድንጋዮች” በሚል ርዕስ በዲያቆን ብርሃኑ አድማስ የወንጌል ትምህርት የተሰጠ ሲሆን የአዲስ አበባ ማእከል የመዝሙር ክፍል አባላት፤ እንዲሁም ተመራቂ ተማሪዎች ያሬዳዊ ወረብና ዝማሬ አቅርበዋል፡፡ በመጨረሻም በዩኒቨርስቲ ቆይታቸው ከፍተኛ ውጤት ላመጡ ተመራቂዎች በማኅበሩ የተዘጋጀላቸውን የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል፡፡

    
     
            

ሰዋሰወ ግእዝ ክፍል ሦስት

ሰኔ 26 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ት ኑኀሚን ዋቅጅራ

ባለፈው ሳምንት አምዳችን ከ፳፮ (26)ቱ የግእዝ ፊደላት መካከል የ፲፫(13)ቱን የግእዝ ፊደላት ቅርጽ ከነትርጒማቸው መግለጻችን ይታወቃል፡፡

ዛሬ ደግሞ ተከታዮቹን አሥራ ሦስት (፲፫) ፊደላት እንመልከት

፲፬. ከ ብሂል- ከሃሊ እግዚአብሔር፡፡
      ከማለት – እግዚአብሔር ሁሉን ቻይ ነው፡፡

፲፭. ወብሂል – ወረደ እም ሰማይ እግዚእነ
      ወ ማለት -ጌታችን ከሰማይ ወረደ፡፡

፲፮. ዐ ብሂል – ዐርገ ሰማያተ እግዚእነ፡፡
      ዐ ማለት – ጌታችን ወደሰማይ ወጣ /ዐረገ/፡፡

፲፯. ዘ ብሂል – ዘኲሎ ይእኅዝ እግዚአብሔር፡፡
      ዘ ማለት -እግዚአብሔር ይይዛል /ሁሉን የሚይዝ ነው/፡፡

፲፰. የ ብሂል – የማነ እግዚአብሔር ገብረት ኀይለ፡፡
      የ ማለት – የእግዚአብሔር ቀኝ ኀይልን አደረገች፡፡

፲፱. ደ ብሂል – ደመረ ሥጋነ ምስለ መለኮቱ፡፡
      ደ ማለት – ሥጋችንን ከመለኮት ጋር አንድ አደረገልን፡፡

፳. ገ ብሂል – ገብረ ሰማያተ በጥበቡ፡፡
     ገ ማለት – ሰማያትን በጥበቡ ሠራ፡፡

፳፩. ጠ ብሂል – ጠዐሙ ወታእምሩ ከመ ኄር እግዚአብሔር፡፡
      ጠ ማለት – የእግዚአብሔርን ቸርነት ታውቁ ዘንድ ቅመሱ፡፡

፳፪. ጰ ብሂል – ጰራቅሊጦስ መንፈሰ ጽድቅ፡፡
      ጰ ማለት – ጰራቅሊጦስ የእውነት መንፈስ ነው፡፡

፳፫. ፀ ብሂል – ፀሐይ ጸልመ በጊዜ ስቅለቱ ለእግዚእነ፡፡
      ፀ ማለት – ጌታ በተሰቀለ ጊዜ ፀሐይ ጨለመ፡፡

፳፬. ጸ ብሂል – ጸጋ ወክብር ተውህበ ለነ፡፡
      ጸ ማለት – ጸጋ እና ክብር ለእኛ ተሰጠን፡፡

፳፭. ፈ ብሂል – ፈጠረ ሰማየ ወምድረ፡፡
      ፈ ማለት እግዚአብሔር ሰማይና ምድርን ፈጠረ፡፡

፳፮. ፐ ብሂል – ፓፓኤል ሥሙ ለአምላክ፡፡
      ፐ ማለት – ፓፓኤል የአምላክ ስም ነው፡፡ 

ከዚህ በመቀጠል ዝርዋን የግእዝ ፊደላትን /የግእዝ ፊደል ዲቃሎች/ ተብለው የሚጠሩትን ፈደላትና በፊደል ገበታ ላይ በስተመጨረሻ ተጽፈው የምናገኛቸውን ፊደላት እንመለከታለን፡፡

  • በፊደል ገበታ ላይ በስተመጨረሻ ተጽፈው የምናገኛቸው ከዋናው የፊደል የአጻጻፍ ቅርጽ ወጣ ያሉ ሁለት ዓይነት ፊደላትን እናገኛለን፡፡

  • ፩ ዲቃሎች /ዝርዋን/ የግእዝ ፊደላት ፪ ዲቃሎች /ዝርዋን/ የአማርኛ ፊደላት በመባል ይታወቃሉ፡፡

ከግእዝ ፊደላት ዝርዝር ጋር የሚሄዱትን የግእዝ ዝርዋን /ዲቃሎች/ ፊደላትን እንመለከታን፡፡

  • ዝርው ማለት ብትን /ቅደም ተከተልን ያልጠበቀ/ ማለት ነው፡፡

  • ዝርዋን የግእዝ ፊደላት ዝርዋን የሚል ስም የተሰጣቸው ከዋናዎቹ የግእዝ ፊደላት ላይ የተወሰነ ቅጥያ እየተጨመረ የተመሠረቱ ፊደላት በመሆናቸው ነው፡፡

  • ዝርዋን መባላቸው እንደ ዋንኞቹ የግእዝ ፊደላት ቅደም ተከተላቸውን ጠብቀው በሰባቱ የፊደላት ዝርዝር ባለመዘርዘራቸውና አብዛኛውን ጊዜ በግእዝ ፊደል በተጻፉ ጽሑፎች ላይ ብቻ መገኘታቸው ነው፡፡ እነዚህ ፊደላት የተመሠረቱት በዋንኞቹ የግእዝ ፊደላት ላይ የተወሰነ ቅጥያ በማድረግ ነው፡፡

  • ዋንኞቹ የግእዝ ፊደላት የአዘራዘር ሥልት በግእዝ ጀምረው በሳብዕ ቅደም ተከተላቸውን ጠብቀው ይዘረዘራሉ፡፡

ምሳሌ፡- ግእዝ      ካዕብ      ሣልስ         ራብዕ      ኀምስ    ሳድስ      ሳብዕ
       ሀ           ሁ          ሂ          ሃ          ሄ           ህ       ሆ    
       ለ           ሉ          ሊ         ላ          ሌ          ል       ሎ

 

የዝርዋን የግእዝ ፊደላት የአዘራዘር ሥልት ግን ከእነዚህ ይለያል

መነሻ ፊደላት

ግእዝ

ሳድስ

ሣልስ

ራብዕ

ኀምስ

 

የዛሬ አምዳችንን በዚህ እናጠናቅቃለን ሳምንት በአማርኛ ፊደላትና ዝርዋን የአማርኛ ፊደላትን የአጻጻፍና የአዘራዘር ሥልት ይዘንላችሁ እስከምንገናኝ ቸር ይግጠመን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

abune endrias

አቡነ እንድርያስ ገዳም/አቡነ እንድርያስ ዋሻ

ሰኔ 21 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

የማኅበረ ቅዱሳን የኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ክፍል አባላት በሰሜንና ደቡብ ጎንደር እንዲሁም በምዕራብ ጎጃም ሀገረ ሰብከቶች በመንቀሳቀስ የአድባራትና ገዳማት እንቅስቃሴዎችን ቃኝተን  ከተመለስን ሰነባበትን፡፡ ክፍል ስድስት ድረስ ጸበል ጸዲቅ በሚል ርዕስ ስናቀርብ መቆየታችን ይታወሳል፡፡ በዚህም መሠረት ቀጣዮቹን ክፍሎች ማቅረባችንን እንቀጥላለን፡፡  

የቴሌቪዥን ክፍል አዘጋጁ ቶማስ በየነ ከቪዲዮ ካሜራ ባለሙያው ሙሉጌታ ቢሆነኝ እኔን ጨምሮ ሊቀ መንኮራኩር ነብያት መንግሥቴ /ማዕረግ የራሳችን/ ሾፌራችን አብራሪነት ከአዲስ ዘመን ከተማ በስተ ሰሜን አቅጣጫ ወደ አቡነ እንድርያስ ዋሻ ገሰገስን፡፡

የአስፋልቱን መንገድ አገባደን ኮሮኮንቹን ጥቂት ወደ ቀኝ ታጥፈን እንደተጓዝን ከፊት ለፊታችን እንደ ጦር የሾሉ ንጣፍ ድንጋዮች አጋጠሙን፡፡ ሊቀ መንኮራኩር ነብያት መኪናውን በንዴት አቁሞ “እንዴት በዚህ መንገድ ላይ ሂድ ትሉኛላችሁ?`ለመኪናው አስቡ እንጂ!” በማለት ከመኪናው ወርዶ በኩርፊያ ከፊት ለፊት ከሚታየው ትልቅ ድንጋይ ላይ ቁጭ አለ፡፡

ያለን አማራጭ በእግር መጓዝ ስለነበር ለቪዲዮ ቀረጻ የሚያገለግሉንን መሣሪያዎች ከመኪናው ላይ አውርደን በመከፋፈል ተሸክመን ጉዟችንን ቀጠልን፡፡ ከአርባ ደቂቃ የእግር ጉዞ በኋላ አቡነ እንድርያስ ዋሻ ደረስን፡፡  የአቡነ እንድርያስ ገዳም ከአዲስ ዘመን ከተማ በስተሰሜን አቅጣጫ ከተራራ ሥር የሚገኝ የዋሻ ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ በአካባቢው በተለምዶ አቡነ እንድርያስ ዋሻ በመባል ይታወቃል፡፡

abune endriasገዳሙ አራት በሮች ሲኖሩት እያንዳንዳቸው ከአንድ  ወጥ እንጨት ተጠርበው የተሠሩ ናቸው፡፡ እያንዳንዱ ደረጃና የበሩ መቃን በጣና ደሴት ውስጥ ከሚገኙት ከደብረ ሲና ማርያም፤ ከደብረ ገሊላ ኢየሱስ አቡነ ዘካርያስ ገዳም፤ ማን እንደ አባ ያሳይ መድኀኔዓለም ገዳም፤ . . . ጋር ተመሳሳይነት አላቸው፡፡ ገዳሙ ምንም ዓይነት እድሳት ያልተደረገለት ሲሆን ጥንታዊነቱን ጠብቆ የሚገኝ የዋሻ ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡  

ቀሲስ ቢራራ በላቸው ይባላሉ፡፡ የገዳሙ አገልጋይና ቁልፍ ያዥ ናቸው፡፡ ስለ ገዳሙ ካጫወቱንና በገዳሙ ውስጥ ከሚገኘው ከአቡነ እንድርያስ ገድል ካገኘነው በጥቂቱ ላቅርብላችሁ፡፡

ቦታው ከክርስቶስ ልደት በፊት በ899 ዓ.ዓ. በዐፄ ባዚን ዘመነ መንግሥት የተመሠረተና የአካባቢው ሰዎች በእንጨት ምስል ቀርጸው ጣዖት እያመለኩ ቆይተውበታል፡፡ ለ440 ዓመታትም የኦሪት መሥዋዕት ሲሠዋበት የነበረ ሲሆን፤ የአካባቢው ነዋሪዎች ዋሻው ውስጥ የሚኖሩ ሁለት ባልና ሚስት  ዘንዶዎችን እርጎ እየመገቡ ያመልኳቸው እንደነበር በገዳሙ ውስጥ የሚገኘው ገድለ አቡነ እንድርያስ ይገልጻል፡፡

በሩን አልፈው ወደ ውስጥ ሲዘልቁ ሰፊውን ቅኔ ማኅሌት ያገኛሉ፤ ከፊት ለፊት ቅድስትና መቅደሱ፤ እንዲሁም በትልቁ የተሳሉ የአቡነ እንድርያስ ስዕሎች ጎልተው ይታያሉ፡፡ በቤተ መቅደሱ ግራና ቀኝ ሰልፋና ደፈር በተባሉ ሰዎች በጥርብ ድንጋይ የተከለሉ ቦታዎች አሉ፡፡ /ሰልፋና ደፈር የዘንዶዎቹ ቀላቢዎች/ እንደነበሩ ገድለ አቡነ እንድርያስን በመጥቀስ አባቶች ይናገራሉ፡፡

ገዳሙ ከክርስቶስ ልደት በኋላም የአካባቢው ሕዝብ ዘንዶዎቹን በማምለክ የቆየ ሲሆን አቡነ እንድርያስ በ13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በአቡነ ተክለ ሃይማኖት በደቀመዛሙርትነት ተመርጠው ምድረ እንፍራንዝ /የአሁኑ ሊቦ ከምከም ወረዳ አካባቢ/ ሄደው ክርስትና እንዲያስተምሩ፤ ህዝቡንም እንዲያጠምቁ ተልከዋል፡፡

አቡነ እንድርያስ ተልእኳቸውን ለመፈጸም ወደ አካባቢው ሲመጡ ረድአቸውን አቡነ ቶማስን አስከትለው ስለነበር አካባቢውን እንዲቃኙና ለጸሎabune endrias 2ት የሚመች ቦታ እንዲፈልጉ ላኳቸው፡፡ ይህ ዋሻ በአቡነ እንድርያስ ረድእ በነበሩት በአቡነ ቶማስ አማካይነት የተገኘ ሲሆን ዘንዶዎቹን ሲመለከቱ በመፍራታቸው ቦታው እንደማይሆናቸውና የዘንዶዎቹን አስፈሪነት ለአቡነ እንድርያስ ይገልጹላቸዋል፡፡ አቡነ እንድርያስም “በእግዚአብሔር ኃይል እናሸንፋቸዋለን” በማለት መጥተው በመስቀላቸው በማማተብ በእግዚአብሔር ስም ይገስጿቸዋል፡፡ በዚህ ቅጽበት አቡነ እንድርያስ የያዙት መስቀል ከመሬት ወድቆ የቀኝ በኩል ክንፉ በመሰበሩ ወደ እግዚአብሔር ቢጸልዩ የእግዚአብሔር መልአክ መጥቶ እንደነበረ አድርጎ ሰጥቷቸዋል፡፡ ከዘንዶዎቹ አንዱ ከአካባቢው ማዶ ተምዘግዝጎ ግራርጌ ጉበያ ማርያም ከሚባል ቦታ ላይ ወድቋል፡፡ አንደኛው ግን እስከ ዛሬ ድረስ የደረሰበት ባይታወቅም ወደ ዋሻው ውስጠኛ ክፍል ገብቶ እንደቀረ ይነገራል፡፡

አቡነ እንድርያስ ገዳሙን አቅንተው የአካባቢው ምእመናንን ክርስትና በማስተማር ታላቅ ተድጋሎ የፈጸሙበት ቅዱስ ስፍራ ነው፡፡ ወደ ገዳሙ በተአምራት አብረዋቸው የመጡ አራት በግምት አንድ ሜትር ቁመት ያላቸውና ከ20 እስከ አሥራ አምስት ሣንቲ ሜትር ስፋት ያላቸው ድንጋዮች መካከል ሁለቱ በደወልነት አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ፡፡ ሲደወሉ ወፍራምና ቀጭን ድምጽ ስለሚያወጡ የወንድና የሴት ደወሎች ይባላሉ፡፡ በአገልግሎት ወቅት ዋሻው ድምጽ እያስተጋባ ስለሚያስቸግር አቡነ እንድርያስ ገስጸውት እስከ ዛሬ ድረስ ዋሻው ምንም ዓይነት ድምፅ አያስተጋባም፡፡

በገዳሙ ውስጥ ዜና ማርያም የተባለችው ቅድስት እናት ለ25 ዓመታት በጸሎት ተወስና ቆይታበታለች፡፡ ከእንጨት ተፈልፍሎ በቁመቷ ልክ በተሠራ ገንዳ ውስጥ ገብታ የገንዳውን ግራና ቀኝ በደረቷ አቅጣጫ በመብሳት በጠፍር በማሰር ትጸልይ ነበር፡፡/ ዜና ማርያም ትጸልይበት የነበረው የእንጨት ገንዳ ዛሬም በገዳሙ ውስጥ ይገኛል፡፡/

በገዳሙ ውሰጥ በጥንቃቄ ጉድለት እየተበላሹ የሚገኙት ቅርሶች እንደ አልባሌ እቃዎች ተጥለዋል ማለት ይቻላል፡፡ ዘንዶው እርጎ ይጠጣበት የነበረው ገንዳ፤ የዜና ማርያም መጸለያ ገንዳ፤ በእንጨት የተሠራ የኦሪት መሠዊያ፤ የመሥዋዕተ በግዕ ሥጋ ማስቀመጫ፤ የደሙ ማኖሪያ፡ ዐፄ ዘርዓያዕቆብ ለገዳሙ ከሰጧቸው 6 ነጋሪቶች መካከል ሁለቱ፤  ብዛት ያላቸው የሰው አጽሞች ይገኛሉ፡፡ ከአጽሞቹ መካከል አንዱ ሙሉ ለሙሉ ሳይፈርስ ከራስ ቅሉ እስከ እግር ጥፍሩ በዘመናዊ ሳጥን ተደርጎ ከላይ በመስታወት ታሽጎ ይታያል፡፡ የአጽሞቹን እድሜ መገመት እንደማይቻልና ቀድሞም እንደነበሩ ቀሲስ ቢራራ በላቸው ይገልጻሉ፡፡

የአቡነ እንደርያስ የእጅ መስቀል በገዳሙ ውስጥ በቅርስነት ተጠብቆ ይኖር እንደነበር፤ ብዛት ያላቸው ምእመናን በመስቀሉ ታሽተው ከያዛቸው ደዌ ይድኑ እንደነበር ቀሲስ ቢራራ በላቸው የዐይን ምስክር እንደሆኑ ይናገራሉ፡፡ ነገር ግን በቅርቡ በአንድ ግለሰብ የአቡነ እንድርያስ መስቀል መዘረፉንና የግለሰቡ ማንነት ታውቆ ክስ ተመሥርቶበት በቀጠሮ ላይ እንደሚገኝ ገልጸውልናል፡፡ የአቡነ እንድርያስን ዋሻ ቆይታችንን አጠናቀን ስንወጣ የገዳሙ አበምኔት የክሱን ሁኔታ ለመከታተል ከሔዱበት ሲመለሱ አግኝተናቸው ነግረውናል፡፡

abune endrias 1ገዳሙ ለስርቆት የተጋለጠ በመሆኑ የገዳሙ ጥንታዊ መጻሕፍት ተሰብስበው በአንድ ታማኝ በሆነ ግለሰብ ቤት ውስጥ እንዲቀመጥ መደረጉንም ቅርሶቹን ለማየት በጠየቅንበት ወቅት ከተሰጠን ምላሽ ለማወቅ ችለናል፡፡ የብራና መጻሕፍት ገድለ ሠማእታት፤ ስንክሳር የዓመት /2/፤ ጸሎተ እጣን፤ ግንዘትና . . . ሌሎችም ንዋያተ ቅዱሳት በዚሁ ታማኝ ነው በተባለው ሰው እጅ ላይ ይገኛሉ፡፡ በየዓመቱም ቆጠራ እንደሚካሔድ በስፍራው ከነበሩት አባቶች ተገልጾልናል፡፡

ምእመናን ተጠምቀው ከተያዙበት ደዌ የሚፈወሱበት ጸበል ከገዳሙ በስተ ደቡብ ይገኛል፡፡ ጸበሉ በምንጭነት የሚፈልቅ ሲሆን ምንም ዓይነት ከለላ ስላልተደረገለት ለከብቶችና ለአራዊት የተጋለጠ ነው፡፡

የኢየሱስ፤ የቅዱስ ሚካኤልና የአቡነ እንድርያስ ታቦታት፤ እንዱሁም የአቡነ እንድርያስ መቃብር በዚሁ ዋሻ ቤተ መቅደስ ውስጥ ይገኛሉ፡፡ አቡነ እንድርያስ ግንቦት 20 ቀን 1246 ዓ.ም. ወደ ገዳሙ እንደገቡ ገድላቸው የሚገልጽ ሲሆን ዓመተ ምሕረቱን ባይገልጽም ጳጉሜ 3 ቀን እንዳረፉ ይጠቅሳል፡፡ገዳሙ ምንም ዓይነት የገቢ ምንጭ የሌለው ሲሆን አገልጋዮቹ የራሳቸውን የእርሻ መሬት እያረሱ በሚያገኙት ይተዳደራሉ፡፡

ስዱዳን ለስዱዳን

ሰኔ 21 ቀን 2005 ዓ.ም

በዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ

ባለፈው ጽሑፌ በገባሁት ቃል መሠረት በባዕድ ምድር የሚኖሩ ወገኖች፤ የስደት ሕይወትን ከጀመሩበት አንሥቶ የጠበቁትን በማጣታቸው ችግር ውስጥ የገቡትን ወገኖቻቸውን እንዴት መርዳት እንዳለባቸው ለመጻፍ አሳቦቼን እያብላላሁ ነበር፡፡ ግንቦት ሃያ ቀን ምሽት እኔና ቤተሰቤ አልፎ አልፎ በምናየው የኢ.ቢ.ኤስ ቴሌቪዥን ጣቢያ አንድ ቃለ ምልልስ ተመለከትኩ፡፡ ቃለ ምልልሱን ያደረገችው በጣቢያው «ሄለን ሾው» የተሰኘ ሳምንታዊ ፕሮግራም ያላት ሄለን አሰፋ ነበረች፡፡ የዕለቱን ውይይት ያደረገችው ትእግሥት ከተባለች በመካከለኛው ምሥራቅ ነዋሪ ከሆነች ኢትዮጵያዊት ጋር ነበር፡፡ ትዕግሥት በወጣትነት የዕድሜ ክልል ውስጥ ትገኛለች፡፡

እንደ ማንኛውም ኢትዮጵያዊት ወጣት ሠርታ ለመለወጥና ቤተሰቦቿን ለመለወጥ ወደ ዐረብ አገር ተሻግራ ለዓመታት የቆየች ናት፡፡ ትዕግሥት ከሄለን ጋር ባደረገችው ውይይት እንደገለጸችው ወደ የመን ከተሻገረች በኋላ እንደ አብዛኛዎቹ እኅቶቻችን በሰው ቤት ተቀጥራ ብዙ ችግሮችን አልፋለች፡፡ በአሠሪዎቿ ምግብ ከመነፈግና ከመራብ ጀምሮ እስከ መደብደብና መታሠር፤ በመጨረሻም እስከ መባረር ደርሶባታል፡፡ ከብዙ ድካም በኋላ በዐረብ አገር የሚሠሩ እኅቶቻችንን ሥቃይ አልፋበት ያየችው ትዕግሥት ላቧን አንጠፍጥፋ ያጠራቀመቻትን ገንዘብ ይዛ በእሷ የደረሰ እንዳይደርስባቸው የኢትዮጵያውያን እኅቶቻችንን ሥቃይ ቢቻል የሚያጠፋ ባይቻል ደግሞ የሚያቃልል ድርጅት ለማቋቋም ትወስናለች፡፡ በዚህ እንቅስቃሴዋ ላይ አንድ መቀመጫውን በኒውዮርክ ያደረገ በስደተኞች ላይ የሚሠራ ድርጅት ጋብዟት ወደ አሜሪካ እንደተሻገረች በቃለ መጠይቁ ገልጻለች፡፡

ትዕግሥት በዐረብ አገር ስለሚገኙ እኅቶቻችንና ሳይፈልጉ ስለሚወልዷቸው ሕጻናት ሥቃይ ስትገልጽ በዕንባም ጭምር ነበር፡፡ በዚያ የሚኖሩ እኅቶች በአጋጣሚ ስሕተት ወይም ተገደው የሚወልዷቸው ሕጻናት የመማርና እንደ ሕፃን የመጫወት መብት ተነፍጓቸው ከወላጆቻቸው ጋር እንደሚመቱ፣ እንደሚራቡና እንደሚታሰሩ ስትገልጽ ሐዘን በሰበረው ድምፅ በዕንባ እየታጠበች ነበር፡፡ ይህች እኅት እነዚህን በከፋ ችግር ላይ ያሉ ሕፃናትና ወላጆቻቸውን ለመርዳት በምታደርገው እንቅስቃሴ በአሜሪካ ያሉ ኢትዮጵያውያን ምን እንዲረዷት እንደምትፈልግ ተጠይቃ አጽንኦትና ትኩረት ሰጥታ የተናገረችው ከወላጆቻቸው ጋር እየተሠቃዩ ያሉ ሕፃናት መጠለያ የሚያገኙበትን፣ ተምረውና እንደ ልባቸው የሚያድጉበትን ዕድል እንፍጠር፤ ወላጆቻቸውንም እንርዳ የሚል ነበር፡፡

ይህ የትዕግሥት መልእክት የዚህ ጽሑፍም የመጀመሪያ መልእክት ነው፡፡ ከብዙ ድካም በኋላ የስደት ሕይወታቸው የሠመረላቸው ኢትዮጵያውያን ወገኖቻቸው በልዩ ልዩ ምክንያት ተሰደው ወደሚኖሩበት አገር ሲመጡ በግልም በማኅበርም ሆነው መርዳት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ለዚህ የተቀደሰ ተግባር ደግሞ በየሚኖሩበት አገር በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጥላ ሥር ተሰባስበው የሚገለገሉና የሚያገለግሉ ምእመናን ምቹ ሁኔታ ተፈጥሮላቸዋል ማለት ይቻላል፡፡ የተቸገሩትን ስለመርዳት፣ ሀገርና ወገንን ስለመውደድና ስለ ፍቅር አብዝታ በምታስተምር ቤተ ክርስቲያን ጥላ ሥር ናቸውና፡፡

ባለፈው ጽሑፋችን እንዳየነው በልዩ ልዩ ምክንያት አገር ወገናቸውን ትተው ወደ ባዕድ ምድር የሚሔዱ ወገኖች ስለሚሰደዱበት አገር ነባራዊ ሁኔታ መረጃ አይሰበስቡም፡፡ በብዛት እንደ ሚታየው ከሔዱም በኋላ በቀላሉ የተለያዩ መረጃዎችን የሚያገኙበት ዕድል የላቸውም፡፡ እንዴትና የት ሥራ እንደሚያገኙ፣ ኑሮአቸው እስከሚ ስተካከልና ራሳቸውን እስከሚችሉ አገሩ ያዘጋጃቸው የዕርዳታ ዕድሎች መኖር አለመኖራቸውን፣ ቋንቋ የትና እንዴት በቀላሉ መማር እንደሚችሉ ወዘተ ቀድመው የሔዱ ኢትዮጵያውያን በግልም በማኅበርም ሆነው ለአዳዲስ ስዱዳን ወገኖቻቸው ማካፈል ይገባቸዋል፡፡ የዚህ ጽሑፍ አዘጋጅ በውጭው ዓለም በነበረው ቆይታ ያረጋገጠው ለአዳዲስ ስዱዳንም ሆነ እዛ በቆዩ ኢትዮጵያውያን መካከል ያለው የመረጃ ልውውጥ ከሌሎች የአፍሪካ ሀገራት በእጅጉ ያነሰ መሆኑን ነው፡፡ ይህ ነገር ወደፊት መሻሻል አለበት፡፡ ወገኗን ብቻ ሳይሆን ባዕዳኑን በየዘመኑ በአክብሮት እየተቀበለች፣ ከገጠማቸው ችግርም እየታደገች ከኖረችና ካለች አገር የሔዱ መሆናቸውን ሊያስታውሱ ይገባል፡፡

የስደት ሕይወት እስከሚለምዱት ድረስ ከባድ ነው፡፡ ተወልደው ካደጉበት ቀዬ፣ ባሕልና ቋንቋ ተለይተው፣ ከቤተሰብ ሙቀትና ክብካቤ ርቀው የሚጀምሩት ሕይወት ነውና፡፡ በብዙ ቦታዎች እንደሚታየው በዚህ ፈታኝ ወቅት ተገቢውን ዕርዳታ ያገኙ ወገኖች በስደት ሕይወታቸው ሁሉ ከወገናቸው ርቀው የሚኖሩ፣ በመንገዳቸው እንኳን ኢትዮጵያዊ ካዩ ወይ መንገድ ቀይረው የሚሔዱ ካልሆነም ሰላምታም ሳይሰጡ የሚያልፉ፣ በጥቅሉ የተገለሉ ናቸው፡፡

በተለያዩ ጊዜያት በልዩ ልዩ መንገዶች እንደ ሰማነው የተሻለ ኑሮ ፍለጋ ረጅሙን በረሐ በሕገ ወጥ መንገድ አቋርጠው፤ ከዚያም አደገኛ በሆነ ሁኔታ ውቅያኖስን አቋርጠው ወደ ጣልያንና ሊባኖስ ይሻገራሉ፡፡ በዚህ ዓይነት ከሚሔዱት ሩብ ያህል የሚሆኑት በመንገዳቸው በሚገጥማቸው አደጋ የበረሃና የውኃ ሲሳይ ሆነው ይቀራሉ፡፡ እግዚአብሔር ጠብቋቸው በረሃውን አልፈው፣ ውቅያኖሱን ዘልቀው ጣልያን የሚደርሱት ወገኖች የተለያዩ ችግሮች ሲያጋጥሟቸው እንደነበር የዚህ ጽሑፍ አዘጋጅ አስተውሏል፡፡ ከሚገጥሟቸው ችግሮች ውስጥ አንዱ በዚያ በሚኖሩ መናፍቃን የሚፈጠርባቸው ችግር ተጠቃሽ ነው፡፡ የጽሑፉ አዘጋጅ በቅርበት እንደተመለከተው በተለይ ጣልያን ያሉ ኢትዮጵያውያን ፕሮቴስታንት አዳዲስ ስዱዳን ወገኖቻችንን በልዩ መንገድ እየተቀበሉ፣ በችግራቸው እየገቡ እምነታቸውን ያስለውጧቸዋል፡፡ ከብዙ ድካምና ሰቀቀን በኋላ ወደማያውቀው አገር የገባ ሰው እንኳን በመልክ የሚመስለው ቋንቋውን እያወራ ልርዳህ ብሎ የቀረበው ሰው አግኝቶ ማንንም ቢሆን መቀበሉ አይቀርም፡፡

በዚህ የተነሣ በጥምቀት ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ ከማኅጸነ ዮርዳኖስ ተወልደው የእናት ቤተ ክርስቲያንን ጡት እየጠቡ ያደጉ ወገኖች፤ በደጇ ተመላልሰው ዕንባቸውን እያፈሰሱ ያደጉባትን ቤተ ክርስቲያን ትተው ሔደዋል፡፡ እየሔዱም ነው፡፡ ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ በዚያ ያለችው ቤተ ክርስቲያን ልጆቿን አስተባብራ፣ ስዱዳን ልጆቿን ተቀብላ ማጽናናትና ማስተናገድ አለመቻሏ ነው፡፡

በደሙ የመሠረታት አምላክ የተመሰገነ ይሁንና ዛሬ ቤተ ክርስቲያችን በዓለም ሁሉ የተበተኑ ልጆቿን እየተከተለች ያልደረሰችበት የዓለም ክፍል የለም፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ ይህንን ሥርጭት ያደረገችው በምናውቃቸው ውስጣዊና ውጫዊ ችግሮች አልፋና እያለፈች እንደሆነ ቢታወቅም ሐዋርያዊ ጉዞዋ ካለው ችግር አንጻር ሲመዘን የሚያስደስት እንጂ የሚያሳዝን አይደለም፡፡ ይሁን እንጂ ምንም እንኳን ሁሉም ናቸው ባይባልም በአብዛኛው አብያተ ክርስቲያናት አገልግሎታቸው በቤተ መቅደስ ብቻ የተወሰነ ነው፡፡ ነገር ግን ቤተ  ክርስቲያን ሐዋርያዊ እጇ ረጅም መሆን አለበት፡፡ በመሆኑም ወደ አካባቢዋ የመጡ ልጆቿን ወዳሉበት ሔዳም የመሰብሰብ አገልግሎት መፈጸም ይጠበቅባታል፡፡ ይህ ተልእኮዋ በተለይ አዲስ ስዱዳንን በመሰብሰብና ከወገናቸው ጋር እንዲተዋወቁ፣ የሀገሩን ባሕልና ቋንቋ እንዲለምዱ ማድረግ ይጠበቅባታል፡፡ ለዚህ ደግሞ በባዕድ ምድር ያሉት አብያተ ክርስቲያናት ይህንን ደገኛና በእጅጉ አስፈላጊ የሆነ ተግባር እንዲያከናውኑ የሚያደርጋቸውን ዕቅድና አሠራር መዘርጋት አለባቸው፡፡

ማጠቃለያ
በጽሑፉ እንደተመለከትነው ሕይወታቸውን በስደት መሥርተው የቆዩ ወገኖች ወደ አካባቢያቸው የሚመጡ ስዱዳንን በመቀበል ሊኖራቸው የሚገባቸውን ሚና በአጭሩ ተመልክተናል፡፡ ከምእመናኑም በተጨማሪ የእነሱ ኅብረት የሆነች ቤተ ክርስቲያንና አስተዳደሯ ይህንኑ ደገኛ ተግባር በመፈጸም ረገድ ልትከተለው የሚገባትን አቅጣጫ አሳይተናል፡፡ በዚህ አጭር ጽሑፍ ከተሰነዘሩት ጥቂት አሳቦች የበለጠ ኑሮአቸውን በስደት ካደረጉ ወገኖች ሊቀርቡ የሚችሉ አሳቦች እንደሚኖሩ ይታመናል፡፡

በመሆኑም በተደጋጋሚ እንደገለጽነው ይህ ዓምድ የተከፈተው ከዝግጅት ክፍሉ ከሚጻፉ ትምህርቶች በተጨማሪ ኑሮአቸውን በውጭው ዓለም ያደረጉ ምእመናን የሕይወት ልምዳቸውንና ተሞክሯቸውን በመለዋወጥ እንዲማሩ ለማድረግ ነው፡፡ ስለዚህ ወገኖቻችን ይህንን ዕድል በመጠቀም አገልግለው በረከት እንዲያገኙ ዛሬም ግብዣችንን እናስተላልፋለን፡፡
 

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት 18 ከሰኔ 1-15 ቀን 2005 ዓ.ም.

ሰዋስወ ግእዝ (ክፍል ሁለት)

ሰኔ 19 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ት ኑኀሚን ዋቅጅራ

 ፩.፪. የግእዝ ፊደላት አካፋፈል

መጀመሪያ ጊዜ ለሄኖስ በጸፍጸፈ ሰማይ (በሰማይ ገበታነት) የተገለጹለት ፊደላት አሁን በፊደል ገበታ ላይ በቅደም ተከተል እንደምናያቸው ሳይሆን ከዚህ በተለየ መልኩ ተዘበራርቀውና የእብራይስጡን የቋንቋ ስልት ይዘው ነው እነሱም አሌፋት በመባል የራሳቸው ስያሜ ነበራቸው

አ – አሌፍ                           ሐ – ሔት                            ሠ – ሣምኬት

በ – ቤት                            ጠ – ጤት                            ጸ – ጻዴ

ገ – ጋሜል                          የ – ዮድ                              ፈ – ፌ

ደ – ዳሌጥ                          ከ – ካፍ                              ዐ – ዔ

ሀ – ሄ                               ለ – ላሜድ                           ቀ – ቆፍ

ወ – ዋው                           መ – ሜም                           ተ – ታው

ዘ – ዛይ                             ነ – ኖን                                ረ – ሬስ

በማለት በእብራይስጡ አጠራር ይጠሯቸው ነበር፤ ነገር ግን እነዚህን የግእዝ ፊደላት በኢትዮጵያ ቀዳማዊ ጳጳስ በአቡነ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን የግእዝ ፊደላትን አሻሽለው አሁን በፊደል ገበታ ላይ የምናያቸውን በቅደም ተከተል ከማስቀመጣቸው በፊት ያሉት ፊደላት፡-

 

ቀዳማዊ የግእዝ ፊደላት በሚል ስያሜ የሚጠሩ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ ከሀ – ጀምሮ በዝርዝር በቀደም ተከተል የምናያቸው ፊደላት ደግሞ ደኀራዊ የግእዝ ፊደላት ብለን በሁለት እንመለከታቸዋለን፡፡

 

፩.፫. ቀዳማዊና ደኀራዊ የግእዝ ፊደላት፣-

፩. ቀዳማዊ የግእዝ ፊደላት የምንላቸው በአሁኑ ጊዜ በፊደል ገበታ ላይ አ፣ በ፣ ገ፣ ደ…./አቡጊዳ/ በማለት የምንጠራው የፊደል አቀማመጥ ነው እነዚህ ፊደላት በመነሻ ፊደል ብቻ ነበር የተጻፉት፡፡

 

                                      ቀዳማዊ የግእዝ ፊደላት

                                      

                                     

                                       

                                     

                                      

                                     

                                      

                                     

                   

በዚህ ዓይነት አቀማመጥ በነጠላ በግእዝ ፊደሉ ብቻ ነበር የተቀመጡት ከዚህ በኋላ ግን በእነዚህ ፊደላት ላይ የተወሰኑ ቅጥያዎችን በመጨመር በመጀመሪያ ደረጃ እነዚህን ፊደላት ወደ ሰባት የፊደላት አዘራዘር በመለወጥ ለእያንዳንዱ ፊደል የተለያዩ ቅርጽና ድምጽን በመፍጠር ፊደላቱ ወደ ሰባት ድምጽ /ሥልት/ ተለውጠው እንዲጻፉ በወቅቱ ከነበሩት ሊቃውንት አባቶች ጋር በመነጋገር የፊደላቱን ቅርጽ አዘጋጅተውልናል፡፡


 

 

ግእዝ

ካዕብ

ሣልስ

ራብዕ

ሐምስ

ሳድስ

ሳብዕ

፲፩

፲፪

፲፫

፲፬

፲፭

፲፮

፲፯

፲፰

 

 

ግእዝ

ካዕብ

ሣልስ

ራብዕ

ሐምስ

ሳድስ

ሳብዕ

፲፱

፳፩

፳፪

፳፫

፳፬

፳፭

፳፮

 

ደሐራዊ የግእዝ (የኢትዮጵያ) ፊደላት አጻጻፍ

 

ግእዝ

ካዕብ

ሣልስ

ራብዕ

ሐምስ

ሳድስ

ሳብዕ

፲፩

፲፪

፲፫

፲፬

፲፭

፲፮

፲፯

፲፰

፲፱

፳፩

፳፪

፳፫

፳፬

፳፭

፳፮

 

የግእዝ ቋንቋ እንደ ሌሎች ቋንቋዎች እራሱን የቻለ ሕግና ሥርዓትን ተከትሎ የሚነገር ጥንታዊ ቋንቋ ነው፡፡ አንድን ቋንቋ እንደ ቋንቋ ከሚያስቆጥሩት መሠረታዊ ነገሮች አንዱ እና ዋንኛው የራሱ የሆኑ ፊደላት ሲኖሩት እና የራሱን የአነጋገር ሥርዓት ተከትሎ መሄድ ሲችል ነው፡፡ ይህም በመሆኑ በዛሬ አምዳችን ስለ ግእዝ ቋንቋ ፊደላት ብዛትና የፊደላቱንም ስያሜ ትርጒም እንመለከታለን፡፡

  1. የግእዝ ፊደላት አጠቃላይ ብዛት ፳፮ (26) ነው፡፡
  2. የግእዝ ፊደላት በሰባት የአዘራዘር ስልት ይዘረዘራሉ፡፡
  3. የግእዝ ፊደላት ብዛት ከነ አዘራዘራቸው ፻፹፪ (182) ናቸው፡፡
  4. ይህም ማለት እየአንዳንዱ ፊደል በሰባት ሥልት ስለሚዘረዘር ነው፡፡

ምሳሌ. ሀ. ግእዝ ሁ. ካዕብ ሂ. ሣልስ ሃ. ራብዕ ሄ.ሐምስ ህ.ሣድስ ሆ. ሣብእ ከፊደል ሀ እስከ ፐ ያሉት ፊደላት በዚህ ዓይነት መንገድ ይዘረዘራሉ፡፡

 

በፊደል ገበታ ላይ የምናገኛቸው የፊደላት ብዛት አጠቃላይ ፴፫ (33) ሲሆኑ ቀሪዎቹ ፯ (ሰባት) ፊደላት የአማርኛ ፊደላት በመባል ይጠራሉ፡፡ እነዚህን ፊደላት ከነ አዘራዘራቸው በሌላ ጊዜ እናያቸዋለን፡፡ ለዛሬ ፳፮ (26)ቱን የግእዝ ፊደላት በቅደም ተከተል ከነትርጒማቸው እንመለከታለን፡፡

 ፩.   ሀ- ብሂል ሀልዎቱ ለአብ እም ቅድመ ዓለም፡፡

   ሀ- ማለት የአብ አኗኗሩ ከዓለም በፊት ነው፡፡

  ፪.  ለ- ብሂል- ለብሰ ሥጋ እምድንግል፡፡

   ለ. ማለት- ክርስቶስ ከድንግል ማርያም ሥጋን ለበሰ፡፡

  ፫. ሐ. ብሂል ሐመ ወሞተ ወተቀብረ፡፡

  ሐ.ማለት ክርስቶስ ታመመ፣ ሞተ፣ ተቀበረ፡፡

  ፬.  መ. ብሂል መንክር ግብሩ ለእግዚአብሔር፡፡

   መ-ማለት የእግዚአብሔር ሥራው ድንቅ ነው

  ፭. ሠ- ብሂል ሠረቀ በሥጋ፡፡

    ሠ- ማለት ጌታ በሥጋ ተወለደ (ተገለጠ)፡፡

  ፮.  ረ- ብሂል ረግዓት ምድር በቃሉ፡፡

   ረ- ማለት ምድር በቃሉ ረጋች (ጸናች)፡፡

  ፯.  ሰ- ብሂል ሰብአ ኮነ እግዚእነ፡፡

    ሰ- ማለት ጌታችን ሰው ሆነ፡፡

    ፰. ቀ- ብሂል ቀዳሚሁ ቃል፡፡

   ቀ- ማለት በመጀመሪያ ቃል ነበር፡፡

   ፱.…….    በ- ብሂል በትኅትናሁ ወረደ እግዚእነ፡፡

   በ- ማለት ጌታችን በትሕትናው ወደኛ ወረደ (ተወለደ)፡፡

        ፲.  ተ- ብሂል ተሰብአ ወተሰገወ፡፡

        ተ- ማለት ጌታችን ሰው ሆነ፡፡

        ፲፩ . ኀ- ብሂል ኀያል እግዚአብሔር፡፡

        ኀ- ማለት እግዚአብሔር ኀያል ነው፡፡

        ፲፪.  ነ- ብሂል ነሥአ ደዌነ ወፆረ ሕማመነ፡፡

 ነ- ማለት ጌታችን ደዌያችንን ያዘልን ሕመማችንን ተሸከመልን

        ፲፫.  አ- ብሂል አአኲቶ ወእሴብሖ ለእግዚአበሔር አቀድም (አእኲቶቶ ለእግዚአብሔር)

                    አ- ማለት እግዚአብሔርን በፍጹም ልቤ አመሰግነዋለሁ (እግዚአብሔርን ማመስገንን አስቀድማለሁ)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

ይቆየን

የስደት ጦስና ተስፋ

ሰኔ 19 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ

ወቅቱ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ለወታደራዊ ሥልጠና ወደ ብላቴ የውትድርና ማሠልጠኛ ጣቢያ እንዲሔዱ የተገደዱበት ነበር፡፡ ተማሪዎቹ በወቅቱ የነበረው መንግሥት ባዘዘው መሠረት ወደ ማሠልጠኛ ጣቢያው ሔደው ለወራት የውትድርናውን ትምህርትና ሥልጠና ወሰዱ፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሔር ጥበቃ ሥልጠናው አልቆ ወደ ጦር ግንባር መወሰጃ ጊዜአቸው ሲደርስ ያዘመታቸው መንግሥት በኃይል ሥልጣኑን ለቀቀ፡፡ በየከፍተኛ ትምህርት ተቋማቱ በአውቶቡስ ተጉዘው ብላቴ በረሃ የከተሙት ተማሪዎች መንግሥት ሲፈርስ የእነሱም ካምፕ ፈረሰ፡፡ ግማሹ ወደየመጣበት ሀገሩ፤ ግማሹ ደግሞ ከሚወዳት እናት ሀገሩ ተለይቶ ወደ ኬንያ ተሰደደ፡፡

ወደ ኬንያ ከተሰደዱት ተማሪዎች አንዱ ክብረት /ትክክለኛ ስሙን ቀይሬዋለሁ/ ነበር፡፡ ክብረት ወደ ኬንያ የተሰደደው ጠላ ጠምቀው በቆልት አብቅለው በመሸጥ ያስተማሩትንና የሚወዳቸውን እናቱን ለመለየት እየጨነቀው ነበር፡፡ ምንም እንኳን ምርጫቸው እንደ አብሮ አደግ ጓደኛቸው ክብረት ወደ ኬንያ መሔድ፤ ከዚያም አውሮፓ¬ ወይም ካናዳ ከተቻለም አሜሪካ መግባት የነበረ ቢሆንም፤ በሁኔታዎች አስገዳጅነት ከብዙ ድካምና ረሃብ በኋላ አገራቸው የገቡት የክብረት ሁለት የሠፈር ልጆች፤ እንደደረሱ ለክብረት እናት በማለዳ ሔደው “እትዬ አበባ /ስማቸው አይደለም/ እንኳን ደስ አለዎት እኛ ፈሪዎች ወደ አገራችን ስንመጣ ደፋሩና ነገን ያሰበው ልጅዎ ኬንያ ገባ፡፡ ራሱን ለውጦ ይለውጥዎታል” ይሏቸዋል፡፡ ይህ አባባላቸው የክብረት ጓደኞች እንዳሰቡት ለእትዬ አበባ የምሥራች አልነበረም፡፡ ድንጋጤው ኡኡታውና ደረት ድቂው ዕድሜ የጎሰመውን አካላቸውን አዝለፍልፎ ለጣላቸው እትዬ አበባ መርዶ ነበር፡፡ ምክንያቱም ለእትዬ አበባ ስደት ማለት ሞት ነው፡፡ እንኳን ጠላ ጠምቀው በመሸጥ ላሳደጉት ብቸኛ ልጃቸው ለማንም ኢትዮጵያዊ ተመኝተውትም አያውቁ፡፡

ይህ በቅርቡ ሃያ ዓመት የሞላው እውነተኛ ታሪክ ነው፡፡ ትላንት የእኛ እናቶች ስደትን እንደሞት ያዩ ነበር፡፡ ተሰደደ/ች ሲሏቸው ሞተ/ች ብለው ያለቅሱ፤ ይጮኹ ነበር፡፡ ወዳጅ ዘመድ ተሰብስቦም ያስተዛዝን ነበር፡፡ ዛሬ ግን ተቀይሯል፡፡ የአንድ ቤተሰብ አባል እንኳን ሔደ ተብሎ፤ የደስታ ድግሱ ፌስታው የሚጀመረው ገና የግብዣ ወረቀት ሲላክ ነው፡፡ የስደት ጉዞው እውን ሲሆን ቪዛ ሲመታለትማ /ሲመታላትማ/ ሰርግና ምላሽ ነው፡፡ ትላንት እነ እትዬ አበባ ልጅዎ ውጭ አገር ሔደ ሲባሉ ልባቸው በሐዘን ተወግቶ ቀሪ ዘመናቸውን በለቀሶና በቁዘማ ፈጽመው ወደ መቃብር ይወርዱ ነበር፡፡ ዛሬ እናት ወይም አባት የልጃቸውን መሰደድ በኩራትና በደስታ ሲናገሩ እንሰማለን፡፡ ለዛሬው ወጣት ወንድሜ ወይም የፍቅር ጓደኛዬ ውጭ አገር ነው ማለት በኩራት የሚናገሩት ስኬት ነው፡፡ ይህ ለምን ሆነ) አንባብያን አሳባችሁን ስጡ፡፡

በየትኛውም መንገድ ወይም ምክንያት በርካታ ኢትዮጵያውያን ሀገራቸውን ትተው በስደት ሕይወታቸውን እንደሚገፉ እርግጥ ነው፡፡ ቁጥራቸው ውጭ ካሉት ወገኖቻችን ቢልቅ እንጂ የማያንስ ኢትዮጵያውያንም እነሱም ውጪ እንዳሉት እንዲሰደዱ ሲጸልዩ፣ ሲሳሉ፣ ገንዘባቸውን ሲያባክኑ፣ ሕይወታቸውን አደጋ ላይ ሲጥሉ እንደሚኖሩ ምስክሮች ነን፡፡ “የውጭ ጉዞዬ እንዲሳካ ቤቱ መጥቼ አልቅሼ ነበር፤ ተሳክቶልኝ አሁን እዚህ እገኛለሁና እልል በሉልኝ” የሚሉ ማስታወቂያዎች በየዐውደ ምሕረቱ እንሰማለን፡፡ “ይህ ደላላ ቪዛ ሊያስመታልኝ ይህን ያህል ሺሕ ብር ሰጥቼው ካደኝ” የሚሉ ፕሮግራሞች በኤፍ ኤም ሬድዮዎቻችንም ጭምር እናደምጣለን፡፡ “ሊቢያ ለመግባት በረሃ አቋርጠው ሲጓዙ የበረሃው ዋዕይ ሕይወታቸውን ቀጠፋቸው፤ የመን ለመግባት በጀልባ ተጭነው ሲቀዝፉ የነበሩ ኢትዮጵያውያን ጀልባቸው በሞገድ ተመትታ በመስጠሟ ሁሉም አለቁ” የሚሉ ዜናዎች በየጊዜው እናነባለን፣ እንሰማለን፡፡ “በዚህ ዐረብ አገር ትሠራ የነበረች ኢትዮጵያዊት በአሠሪዋ አሲድ ወይም የፈላ ውኃ ተደፋባት፤ ከፎቅ ተወረወረች፤ አስከሬኗ መጣ” የሚሉ መርዶዎች መስማት ልማዳችን ሆኗል፡፡ ይህ ሁሉ ለምን ሆነብን) አንባብያን አሳባችሁን፤ ገጠመኞቻችሁን የደረሰባችሁን ሁሉ ወደ ዝግጅት ክፍሉ ላኩ፡፡

በልዩ ልዩ ምክንያት ከሀገር ወጥተው ከውቅያኖሱ ባሻገር ከሚኖሩት ወገኖቻችን በዕውቀታቸውና በሙያቸው አገሩ ፈልጎአቸው በስኬት የሚኖሩ ያሉትን ያህል፤ ኑሮ ከሀገሩ እንግዳ ባሕልና የአየር ጠባይ የበለጠ ከብዶአቸው በምሬትና በመሳቀቅ የሚኖሩ፤ አልፎ አልፎም ራሳቸውን የሚያጠፉ እንዳሉ እንሰማለን፤ እናያለንም፡፡ ይህ ችግር በተለይ ገና የስደቱን ኑሮ አሐዱ ብለው በጀመሩት ይበዛል፡፡ ከብዙ ጸሎትና ድካም በኋላ ያሰቡት ተሳክቶ የሔዱ ወገኖች የቅርብና የልብ ወዳጅ ዘመድ ካጠገባቸው ከሌለ ከፍተኛ ችግር ውስጥ ይገባሉ፡፡ ብዙ ጊዜ እንደምንሰማው ገና እንደሔዱ የሚያጋጥማቸው ችግር ሕሊናቸውን ከመጉዳቱ ባሻገር ጠባሳው በስደት ሕይወታቸው ሁሉ ዘልቆ ኑሮአቸውን ከባድ ያደርግባቸዋል፡፡

የሥነ ልቡና ምሁራን አንድ ሰው የጠበቀውን እና የጓጓለትን ነገር ሲያጣ የሚያጋጥመውን ሥነ ልቡናዊ ስብራት ሥነ ልቡናዊ መራቆት /Psychological Crisis/ ይሉታል፡፡ በአገራቸው ምድር ሳሉ ሁሉም ለምለም ሆኖ በምናብ ይታያቸው የነበረ የባዕድ ምድር፤ ምድሩ ላይ ቆመው ሲያዩት ልምላሜው በቀ ላሉ ምግብ የማይሆን ሆኖ ሲያገኙት፤ በአጭሩና ካለ ብዙ ድካም በኪስ እንደሚታጨቅ ያሰቡት ገንዘብ ብዙ ድካምና ራስን ዝቅ ማድረግ እንደሚጠይቅ ሲረዱ ከፍተኛ ጭንቀት ውስጥ ይገባሉ፡፡ ጭንቀታቸው በርትቶም የጤና እክል ይገጥማቸዋል፡፡ ይህ የጤና ችግር ደግሞ በስደቱ ምድር በጉልበታቸው ሮጠው በዕውቀታቸው ተወዳድረው ሕይወታቸውን እንዳያሻሽሉ ዕንቅፋት ይኾንባቸዋል፡፡ ለመሆኑ በርካታ ኢትዮጵያውያን የስደትን ሕይወት ሲጀምሩ ከፍተኛ መደናገጥ፣ መታመምና አልፎ አልፎም ኅልፈተ ሕይወት የሚያጋጥማቸው ለምንድን ነው) የተወሰኑትን ምክንያቶች ከዚህ በታች እናያለን፡፡

1. የተሳሳተ መረጃ
ሀገር ቤት ያለን ኢትዮጵያውያን ስለውጭው ዓለም የምንረዳው በዋና ነት በዚያ ከሚኖሩ ወገኖቻችን ነው፡፡ ምንም እንኳን የባዕድ ሀገር ሕይወት ምን ዓይነት እንደሆነ ካዩትና ከደረሰባቸው እውነቱን የሚናገሩ ቢኖሩም፤ በአብዛኛው በስደት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ለዕረፍት ወደ ሀገራቸው ሲመጡም ሆነ እዚያው ባሉበት ሆነው ለወዳጅ ለዘመዳቸው የሚያስረዱት፤ በእጅጉ እንደሚመች፣ ሰው ዐቅሙ እስካለው ድረስ ሥራ አማርጦ በመሥራት ገንዘብ እንደሚዛቅበት ነው፡፡ ለዚህ ከእውነት የራቀ ምስክርነታቸው ማስረጃ ለማድረግም ብዙ ደክመው /በግሌ እንዳየሁትም/ ለራሳቸው በአግባቡ ሳይመገቡና ሳይለብሱ ያጠራቀሟትን ገንዘብ ወደዚህ ሲልኩ ጥቂቷና በብዙ ድካም ያገኟት ገንዘብ በሀገራችን ምንዛሬ በርክታ ከወዳጅ ዘመድ እጅ ስትገባ የስደት ሀገሩን ለምለምነት ትሰብካለች፡፡ በፎቶ ግራፍ ተቀርጾ የሚላከው በረጅሙ ወርኃ በረዶ ወቊር የገረጣ ፊት ሀገር ቤት ለሚኖረው ሰው የባዕድ አገር ሕይወትን ምቾት የሚሰብክ ነው የሚመስለው፡፡

በሀገራችን የዲዮስጶራ ሰርግ የሚባል አለ፡፡ የዲዮስጶራ ሰርግ አንድ ወይም ሁለቱ ተጋቢዎች ከውጭ መጥተው ጋብቻቸውን የሚፈጽሙበት ሰርግ ነው፡፡ ይህንን ሰርግ ልዩ የሚያደርገው /ሁሉም ማለት አይደለም/ ወጪው በእጅጉ የበዛ፤ የሰርጉ ታዳሚዎች እስከሚሰለቻቸው ድረስ መብል መጠጡና የመናፈሻው ሥርዓት የበዛ፣ ሙሽሮች የሚሞሸሩበት መኪናም ጭምር ከሰማይ የወረዱ እስከሚመስል ድረስ ለታዳሚ ዓይን ግራ የሚያጋባ፤ በጥቅሉ “የናጠጠ” ሰርግ መሆኑ ነው፡፡ ይህንን ያየ ወጣት ታዳሚ በሀገሩ በድሎት የሚኖርም ቢሆን እንኳ እሱም ባሕር ማዶ ተሻግሮ በመሥራት በልጽጎ በመመለስ በተመሳሳይ ሁኔታ ማግባትን ይመኛል፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ የብዙዎች ዲዮስጶራ ተጋቢዎች የውጭ ሕይወት እዚህ መጥተው ሰርጋቸውን ድል ባለ ሁኔታ እንደደገሱለት አይደለም፡፡ ነገር ግን ያላቸውን ካሟጠጡ በኋላ ከሌላውም ተበድረው ድል ያደርጉታል፡፡ ይህ ከእውነታ ውጭ የሆነ የዲዮስጶራ ወገኖቻችንን የውጭ አገር ገለጻና ካላቸው በላይ ገንዘብ መርጨት ሲያዩና ሲሰሙ የቆዩ ወገኖች እነሱም ዕድሉን አግኝተው ሲሔዱ፤ ያ በርቀት የሳሉት የባዕድ ምድርና ሕይወት እንዳልጠበቁት ሆኖ ሲያገኙት ከፍተኛ የመንፈስ ስብራት ያጋጥማቸዋል፡፡

2. የገቡት ቃል
ኢትዮጵያውያን የስደት ሕይወት እንደጀመሩ ለከፍተኛ የመንፈስ ስብራት የሚዳርጋቸው ሌላው ምክንያት ሀገራቸውን ከመልቀቃቸው በፊት ለወዳጅ ዘመዳቸውና ጓደኛቸው ገብተውት የሚሔዱት ቃል ኪዳን ነው፡፡ ከላይ ባየነው መልኩ ወደ ውጭ እንደሔዱ በገንዘብ ባሕር ላይ የሚሰጥሙ ይመስላቸውና ለቪዛው ፕሮሰስና ለትራንስፖርት እንደሁም ለሽኝት ድግስ ብዙ ብር ይበደራሉ፡፡ ወደውጭ ለሚሔድ የሚያበድር አይጠፋምና፡፡ ከዚህም በተጨማሪ አብረዋቸው ሲቸገሩ ለኖሩት ወላጆቻቸውና ዘመዶቻቸው ከፍተኛ የዕርዳታ ተስፋ ይሰጣሉ፡፡

ይሁን እንጂ ብዙ ጊዜ እንደሚታየው የስደት ሕይወት እንደተጀመረ ከተሻለ ኑሮ ላይ አያፈናጥጥም፡፡ ተሰዳጁ ሥራ ያዘም አልያዘ ከገባበት ቀን ጀምሮ ውጭ ስላለው ሕይወት አስቀድሞ በመረዳት ራስን አሸንፎ መሠረት ለማስያዝ ረጅም ጊዜ ይወስዳል፡፡ በዚህ ስደት ተሰዳጁ ሀገሩ ትቶት የመጣውን ቃልኪዳን እያሰበ፤ አብረውት ሲቸገሩ የነበሩ ቤተሰቦቹን ጉጉትና ጠኔ በሕሊናው እየሳለ ይጎዳል፡፡ ጉዳቱም የመንፈስ ስብራት ይሆንና ሠርቶ ሊያገኝበት ከሀገሩ ይዞት የሔደው ጉልበት እየደከመ በሽታ ላይ ይወድቃል፡፡ ይህ ጉዳት እንዲደርስበት ያልፈለገ ደግሞ ገንዘብን በአቋራጭ ለማግኘት ሲል ኢትዮጵያዊ መልኩና የሀገሩ ሕግ በማይፈቅድለት ተግባር ተሠማርቶ የባሰ ችግር ላይ ይወድቃል፡፡

3. አለመዘጋጀት
እንኳን ለቀዋሚ ኑሮ ይቅርና ለጊዜያዊ ዕረፍት ወይም ሥራ የሚደረግ ጉዞ ከፍተኛ ዝግጅትን ይጠይቃል፡፡ ከዝግጅቶቹ ውስጥ ስለሚሔዱበት ሀገር ባሕል፣ ቋንቋና አሠራር ማወቅ መሠረታዊ ጉዳይ ነው፡፡ ብዙ ጊዜ እንደሚታየው በርካታ ወገኖቻችን ወደ ውጭ የመሔድ ዕድል ሲያጋጥማቸው፤ ለራሳቸውና በዚያ ለሚያገኟቸው ዘመ ዶች የሚያካፍሉት ሽሮና በርበሬ እየሸ ከፉ በአውሮፕላን ገብተው የሚበሩባትን ቀን በጉጉት ከመጠበቅ ባለፈ ሁኔታ ዝግጅት አያደርጉም፡፡ በዚህም የተነሣ እንደሔዱ ከፍተኛ ድንጋጤና ሥነ ልቡናዊ ጫና ውስጥ ይገባሉ፡፡ ሥራ ለመፈለግ የሀገሩን ቋንቋ በሚገባ አላወቁም፣ በነጻነት ለመንቀሳቀስ አስቀ ድመው ስለሀገሩ አነዋወርና ሕግ አላጠኑም፡፡ ይህ ዓይነት ችግር በተለይ ኢትዮጵያውያን በማይበዙባቸው ሀገራት ጎልቶ ይታያል፡፡

ኑሮአቸውን በስደት የሚጀምሩ ወገኖች ለወዲያው ለሚያጋጥማቸው የሕሊና ስብራት ምክንያቶቹ እነዚህ ብቻ አይደሉም፡፡ ለአብነት ያህል ከተጠቁሱት የምንገነዘበው ግን የስደት ሕይወት ሀገር ላይ ተቀምጦ እንደሚያስ ቡት የተመቻቸ /የተደላደለ/ እንዳልሆነና የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶች እንዳሉ በመረዳት ተዘጋጅቶ መሔድ እንደሚገባ ነው፡፡ በሚቀጥለው ዕትም በተለይ የስደት ሕይወትን የሚመሩ ወገኖች ከሚደርስባቸው ሥነ ልቡናዊ ስብራት ለመታደግ በዚያ ካለችው ቤተ ክርስቲያንና ምእመናኗ ምን ይጠበቃል) የሚለውን እንመለከታለን፡፡ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ያላችሁ ምእመናን የሕይወት ተሞክሯችሁንና ለሌላው ትምህርት ይሆናል የምትሉትን በዝግጅት ክፍሉ የስልክና የፖስታ ሳጥን ቁጥር፣ በኢሜይል እንዲሁም በአካል እየመጣችሁ እንድታደርሱን በአክብሮት እንጋብዛለን፡፡

መፍትሔዎች፡-

  1. በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ስለሚኖሩበት ምድርና ሕይወት ሳይጨምሩና ሳይቀንሱ እውነቱን በአገር ቤት ለሚኖሩ ወዳጅ ዘመዶቻቸው ይግለጹ፡፡ ሥራ ለማግኘት ምን ያህል ርቀት እንደሚጓዙ፣ ከብዙ ድካም በኋላ ስለሚያገኙት ገንዘብ፣ በወር ስለሚሸፍኑት ቢል ብዛት፤ ስለአየር ጠባዩ፣ ስለ አሠሪና ሥራ ግንኙነት፣ ስለ ቤተሰብ ሕይወት ወዘተ. . . በግልጽ ቢናገሩ ወገኖቻችን በመጓጓትና ትልቅ ነገርን በመጠበቅ ሔደው ከመደንገጥ፣ ከበሽታ ነጻ ይሆናሉ፡፡

  2. በተለያየ ምክንያት ሀገራቸውን ለቀው የሚሔዱ ሰዎች በተቻላቸው መጠን የሚሔዱበትን ሀገር እንደሀገራቸው ሁሉ የራሱ ተግዳሮት የሌሉት፣ ሁሉም ነገር አልጋ በአልጋ እንደሆነ አድርገው መሣል የለባቸውም፡፡ ይህንን ካደረጉ ለቀሪ ዘመዶቻቸው የሚገቡት ቃል አይኖርም፡፡ ቢኖርም ሊያጋጥም የሚችለውን ተግዳሮት ግንዛቤ ውስጥ የከተተ ይሆናል፡፡

  3. ኑሮአቸውን በባዕድ ምድር ለማድረግ ወስነው የሚሔዱ ወገኖች አስቀድሞ ልዩ ልዩ ዝግጅቶችን ማድ ረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡ እዚያ ሲሔዱ ከሚበሉትና ከሚጠጡት በተጨማሪ ሀገሩ ምን ዓይነት የአየር ጠባይ አለው) ቋንቋውን በሚገባ አውቀዋለሁን) ሕግጋቱና የአነዋወር ይትበሃሉ ሁሉ ምን ይመስላል) ወዘተ ለሚሉት ጥያቄዎች በቂ ምላሽ መያዝ /ማዘጋጀት/ ይገባቸዋል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር  

 

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት 17 ከግንቦት 16-30 ቀን 2005 ዓ.ም.

ጰራቅሊጦስ (ለሕፃናት)

ሰኔ 14 ቀን 2005 ዓ.ም.

በቤካ ፋንታ

 

  • እግዚአብሔር የሠራት ቀን ይህች ናት/ መዝ 118፥24/

ይህች ታላቅ ዕለት  ከቅድስት ሥላሴ አንዱ አካል የሆነው እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ለቅዱሳን ሐዋርያት፣ ለቅዱሳን አርድእትና ለቅዱሳት ሴቶች የተገለጠባት ዕለት ናት፡፡    እነዚህ ሁሉ በጸሎት ተግተው በሚጸልዩበት ወራት መንፈስ ቅዱስ  በተከፋፈሉ የእሳት ልሳን አምሳል የወረደበት ቅዱስ ቀን ነው፡፡

አስቀድሞ ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱሳን ሐዋርያት ደብረ ዘይት በተባለ ታላቅ ተራራ ላይ ሳሉ እንዲህ ብሎ አስተምሯቸው ነበር “ኀይልን ከላይ ከአርያም እስክልክላችሁ ድረስ በኢየሩሳሌም በጸሎት ቆዩ፡፡”/ሉቃ 24፡36/ መቶ ሃያው ቤተሰብም በኢየሩሳሌም ሀገር በምትገኝ በቤተ መቅደስ በአንድነት ሆነው በጸሎት በመትጋት ቆዩ፡፡ ልጆችዬ መቶ ሃያው ቤተሰብ የሚባሉት 12ቱ ሐዋርያት፣ 72ቱ አርድእት/አገልጋዮች/ እና 36ቱ ቅዱሳን አንስት/ሴቶች/ ናቸው፡፡

ከዕርገት በኋላ በአሥረኛው ቀን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ሐዋርያት ወዳሉበት፣ በጸሎትና በምሥጋና ወደ ሚተጉበት ሥፍራ በእሳት አምሳል /ምሳሌ/ ወርዶ በእያንዳንዳቸው ላይ ተቀመጠባቸው፡፡ ይሄንንም  ሁኔታ ተከትሎ  ምስጢር ተገለጠላቸው፣ ይፈሩ የነበሩት ሐዋርያትም ወንጌልን ለማስተማር ደፋሮች ሆኑ፣ በተለያየ ቋንቋዎች እንዲናገሩ እውቀት ተሰጣቸው፤ የእግዚአብሔርንም ጸጋ ተቀበሉ፡፡ ይህንን ታላቅ ኀይል እና ሰማያዊ ስጦታን የሰጣቸውን እግዚአብሔርን በታላቅ ዝማሬና እልልታ አመሰገኑት፡፡

በዓለ ሃምሳ የሚባለውን የአይሁድን በዓል ለማክበር ከተለያዩ ሀገራት የመጡ በጊዜው  የነበሩ ቁጥራቸው በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ  ሰዎች የሐዋርያቱን ታላቅ የዝማሬና የእልልታ ድምፅ ሰሙ፡፡ ከመቶ ሃያው ቤተሰብ መካከል አንዱ የሆነው  ቅዱስ ጴጥሮስ የተሰበሰቡት ሁሉም እንዲሰሙት ድምፁን ከፍ አድርጎ ቃለ እግዚአብሔርን እንዲህ ብሎ አስተማራቸው፡፡ “እናንተ የእስራኤል ሰዎች ሆይ እኛን የሰው ልጆችን ለማዳን እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆኖ ወደ ምድር መጥቶ ከክፉ ሥራ ተመለሱ፣ ኀጢአትን አታድርጉ፣ በቅድስና ኑሩ፣ ወደ እኔም ተመለሱ ቢላችሁ፤ እናንተ ግን ምንም በደል ሳይኖርበት ገረፋችሁት፣ አንገላታችሁት፣ በመስቀል ላይም ሰቀላችሁት፡፡ እርሱ ግን እግዚአብሔር ነውና ሞትን ድል አድርጎ ተነሣ፡፡ እርሱ ግን አሁንም ይቅር ባይ ነውና ከኀጢአታችሁ ተመለሱ ንስሐም ግቡ ፡፡” በማለት አስተማራቸው፡፡

የተሰበሰቡት ሰዎች ሁሉ ተገረሙ፡፡ ምክንያቱም ሐዋርያት በፊት የሚያውቁት አንድ ቋንቋ ብቻ ነበረ፡፡ በዚህ ሰዓት ግን ሰባ ሁለት ቋንቋን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ገልጦላቸው ለሁሉም በየቋንቋቸው አስተማሯቸው፡፡ ይህንንም ድንቅ ተአምር ከተመለከቱት ብዙዎች እግዚአብሔርን አመሰገኑት፡፡ ወደ ሐዋርያትም ቀርበው “አባቶቻችን እናንተ የእግዚአብሔር አገልጋዮች ናችሁና ምከሩን፡፡ እንደ እናንተ የእግዚአብሔር ልጆች እንድንሆንና በቅድስና እንድንኖር ምን እናድርግ?”በማለት ጠየቁ፡ በዚያች ቀን ቁጥራቸው  ሦስት ሺ ያህል ሰዎች በቅዱስ ጴጥሮስ ትምህርት አምነው  ክርስቲያን ለመሆን ቀረቡ፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም እንዲህ አላቸው፡፡ “እነሆ ሁላችሁም ንስሐ ግቡ፡፡ በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት አምናችሁ ተጠመቁ፡፡” አላቸው በዚያው ዕለትም ሦስት ሺ ሰዎች ወደ ሐዋርያት በመቅረብ ኀጢአታቸውን ተናገሩ፤ ሐዋርያትም እግዚአብሔር ይፍታችሁ እያሉ ልጅነትን የሚያሰጣቸውን ጥምቀት አጠመቁዋቸው፡፡

ከዚያ ቀን ጀምሮም በየዓመቱ ይህችን ታላቅ የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን የምትባለውን በዓለ ጰራቅሊጦስን ክርስቲያኖች በታላቅ ደስታና ምሥጋና እናከብራታለን፡፡ እናንተም ልጆችዬ እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት በቤተ ክርስቲያን ተገኝታችሁ ቅዳሴ በማስቀደስ፣ መዝሙር በመዘመር እና በመጸለይ ይህችን ታላቅ በዓል ልታከብሯት ይገባል፡፡

የእግዚአብሔር አብ ጸጋ የእግዚአብሔር ወልድ ቸርነት የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ አንድነት ከሁላችን ጋር ይሁን  አሜን፡፡

በባዕድ ምድር እስከመቼ?

ሰኔ 14 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ

የስምዐ ጽድቅ ዝግጅት ክፍል በዝርወት ለሚኖሩት የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆች የእናት ቤተ ክርስቲያናቸውን አስተምህሮ፣ ምክርና ተግሳጽ ይሰሙ ዘንድ ዓምድ በከፈተላቸው ጊዜ፤ መጀመሪያ ወዲያውም ዓምዱን ማስተዋወቂያ  ቢሆን ብዬ የጻፍኩት ጽሑፍ ዐራት እትሞች ዘልቆ ተፈጸመ፡፡ ጽሑፉን አስመልክቶ ከተለያዩ ጓደኞቼ ካገኘሁአቸው አስተያየቶች በመነሣት እንደ አብርሃም ሁሉ የያዕቆብን የስደት ሕይወት በመመርመር ለዛሬዎቹ ስዱዳን አርኣያ በሚኾን መልኩ በአጭሩ ለማቅረብ መረጥኩ፡፡ ጽሑፉ ይኸውና፡፡ በዚሁ አጋጣሚ ግን ኑሮአቸውን በስደት ያደረጉ ወንድሞችና እኅቶች ዕለት ከዕለት ከሚያጋጥማቸው ችግር በመነሣት ጽሑፎችን አዘጋጅተው ወደ ዝግጅት ክፍሉ በመላክ ቢማማሩ መልካም ነው፡፡

ሕይወተ ያዕቆብ
ከአያቱ አብርሃምና አባቱ ይስሐቅ ቀጥሎ ሦስተኛው የሕዝበ እስራኤል አባት /3rd Patriarch/ ተብሎ የሚታወቀው ያዕቆብ ወላጆቹ ይስሐቅና ርብቃ በጋብቻ በተጣመሩ ሃያኛው ዓመት ላይ ተወለደ፡፡ እሱ ሲወለድ አባቱ የ60 ዓመት ጎልማሳ ነበር፡፡ /ዘፍ. 25ሚ20፤ 25ሚ26/፡፡ ይስሐቅና ርብቃ በሃያ ዓመት የጋብቻ ሕይወታቸው ወልደው ለመሳም አልታደሉም ነበር፡፡ በዚህ የተነሣም የአብራካቸው ክፋይ የሆነ ፍሬ ይሰጣቸው ዘንድ አምላክን ይማጸኑ ነበር፡፡ እግዚአብሔር ጩኸታቸውን ሰምቶ በርብቃ ማኅፀን ያዕቆብና መንትያው ኤሳው ተፀነሱ፡፡ ነገር ግን በልመናና በጩኸት የተፀነሱት ያዕቆብና ኤሳው ገና በማኅፀን ውስጥ ሳሉ እየተገፋፉ እናታቸውን ይሠቃዩ ጀመር፡፡ በዚህ የተሠቃየችው ርብቃ እንደ ገና ፅንሱን ወደ ሰጣት አምላክ ምሕረትን በመለመን ጮኸች፡፡ በዚህ ጊዜ በማኅፀኗ የተቀረጹ ልጆቿ እስከሚወለዱና ከተወለዱም በኋላ ዕድሜ ልካቸውን የሚጣሉና አንዱ በሌላው ላይ እየተነሣ እንደሚጥለው በራእይ ተረዳች፡፡ ይህንን ምስጢር በልቡናዋ ያዘችው እንጂ ለባሏ አልነገረችውም ነበር፡፡ ሕፃናቱ ሲወለዱ እንደተነገረው ትንቢት አንዱ ከሌላው የማይመሳሰል ሆነው ተወለዱ፡፡ በኲሩ ዔሳው እንደ ጽጌረዳ አበባ ሰውነቱ ሁሉ ቀይና ጸጉራም ሆኖ፣ በኋላ የተወለደው ያዕቆብም የወንድሙ የዔሳውን እግር ይዞ ወደዚህ ዓለም መጡ፡፡ የኋለኛው በዚህ ግብሩ ያዕቆብ ተብሏል፡፡

 

ያዕቆብ ብሂል አኀዜ ሰኰና አዕቃፄ ሰኰና ማለት ነው፤ ሲያድጉም ዔሳው የበረሃ ሰው አርበኛ አዳኝ ሲሆን ያዕቆብ ግን ጭምት ሰው ነበር፤ በድንኳንም ይቀመጥ ነበር፡፡ ዔሳው አድኖ በሚያመጣለት ምግብ የተነሣ የአባቱን ከፍ ያለ ፍቅር ሲያገኝ ያዕቆብ ደግሞ ከቤት ውሎ እናቱን ስለሚያጫውትና ስለሚታዘዛት የእናቱን ከፍ ያለ ፍቅር አገኘ፡፡ አባታቸው ይስሐቅ በእርጅና ምክንያት ጉልበቱ ደክሞ ዓይኑ ደግድጎ ከቤት በዋለ ጊዜ አንድ ቀን የሚወደውን ልጁን ዔሳውን እኔ እንደ ምወደው አድርገህ የምበላው አዘጋጅተህ እበላ ዘንድ ሳልሞት ሰውነቴ /ነፍሴ/ እንድትመርቅህ /እንድትባርክህ/ ወደ ዱር ሄደህ አድነህ አምጣልኝ አለው፡፡ ይህንን የሰማች ርብቃም የምትወደውን ልጇን ያዕቆብን እንደ ዔሳው አስመስላ አልብሳ አባቱ ይስሐቅ የጠየቀውን ምግብ እንደሚወደው አድርጋ አዘጋጅታለት ይዞ ወደ አባቱ እንዲገባና የአባቱን በረከት እንዲቀበል የምትችለውን ሁሉ በማድረግ አዘጋጀችው ዔሳውን መስሎ ወደ አባቱ በመግባትም የአባቱን በረከት ለመቀበል በቃ፡፡ በረከት በመቀበል እንደቀደመው የተረዳው ወንድሙ ዔሳውም “በጽድቅ ተሰምየ ያዕቆብ እስመ ፪ ጊዜ አዕቀጸኒ  ቀዳሚ ብኲርናየ ነሥዓኒ ወናሁ ዮምኒ ወዳግመ በረከትየ፤ ያዕቆብ በእውነት ስያሜውን አገኘ፡፡ አንደኛ ብኲርናዬን ሁለተኛ በረከቴን ወስዶብኛልና ሁለት ጊዜ አሰነካክሎኛ” በማለት ምሬቱን ገልጿል፡፡ /ዘፍ.27፥6/ ያም ሆነ ይህ ሁሉም በፈቃደ እግዚአብሔር የተከናወነ ሆነ፡፡

ምክንያተ ስደቱ
ለያዕቆብ ስደት ምክንያት ከሆኑት ጉዳዮች አንዱ ትዳር ነው፡፡ በቅዱስ መጽሐፍ አባቱ ይስሐቅ ያዕቆብን ጠርቶ መርቆ “ከከነዓን ሴቶች ልጆች ሚስት አታግባ፡፡ ተነሥተህ በጤግሮስና በኤፍራጥስ መካከል ወደሚኖር ወደ እናትህ አባት ወደ ባቱኤል ቤት ሒድ፡፡ ከናትህ ወንድም ከላባ ልጆች ሚስት አግባ ብሎ አዘዘው፡፡ ፈጣሪዬ ካንተ ጋራ በረድኤት ይኑር፡፡ ያክብርህ ያግንህ ያብዛህ፡፡ ብዙ የብዙ ወገን ያድርግልህ አለው፡፡ እግዚአብሔር ለአብርሃም የሰጠውን ምድር ከነዓንን ትወርሳት ዘንድ የአባቴ የአብርሃምን በረከት ይስጥህ፡፡ ካንተ በኋላ ላሉ ለልጆችህም ይስጣቸው” አለው፡፡ /ዘፍ.28፥1-5/

ከያዕቆብ ሕይወት ምን እንማራለን?
ሀ. የእግዚአብሔርን ውለታ እያሰቡ ፍቅርን በሥራ መግለጽ
ያዕቆብ በስደት ሕይወቱ እግዚአብሔር በተለያዩ ጊዜያት እየተገለ ጠለት መክሮታል፤ አበረታቶታል፤ ሲያጠፋም ገሥጾታል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ያዕቆብ አባቱ ይስሐቅ “ከከነዓናውያን ሴቶች ልጆች ሚስት አታግባ፤ ተነሣና ወደ እናትህ አባት ወደ ባቱኤል ቤት ወደ ሁለቱ ወንዞች መካከል ሒድ፤ ከዚያም ከእናትህ ወንድም ከላባ ሴቶች ልጆች ሚስትን አግባ፡፡ ሁሉን የሚችል አምላክም ለብዙ ሕዝብ ጉባኤ እንድትሆን ይባርክህ ያፍራህ ያብዛህ ስደተኛ ሆነህ የተቀመጥህባትን እግዚአብሔርም ለአብርሃም የሰጣትን ምድር ትወርስ ዘንድ የአብርሃምን በረከት ለአንተ ይስጥህ ለዘርህም እንዲሁ እንደ አን” ብሎ ምክር ያዘለ ትእዛዝ በሰጠው መሠረት ከቤርሳቤህ ተነሥቶ የርብቃ ወንድም ላባ ወደ ሚገኝበት በሁለቱ ወንዞች መካከል ወደምትገኝ ወደ ሶርያ ጉዞ ጀመረ፡፡ ሲጓዝ ውሎ ሎዛ ተብላ ትጠራ ከነበረች ቦታ ሲደርስ መሸበት፤ ደከመውም፡፡

 

በዚያውም ድንጋይ ተንተርሶ ተኛ፡፡ በሕልሙም መሰላል በምድር ላይ ተተክሎ ራሱም ወደ ሰማይ ደርሶ በመሰላሉም የእግዚአብሔር መላእክት ሲወጡበትና ሲወርዱበት ተመለከተ፡፡ በመሰላሉ ላይ የቆመው እግዚአብሔርም “የአባትህ የአብርሃም አምላክ የይስሐቅም አምላክ እኔ እግዚአብሔር ነኝ፤ ይህችን አንተ የተኛህባትን ምድር ለአንተም ለዘርህም እሰጣለሁ፤ ዘርህም እንደ ምድር አሸዋ ይሆናል፤ አሕዛብ ሁሉ በአንተ ይባረካሉ፤ ይከብራሉ፡፡ ያዕቆብን ያከበረ ያክብርህ እየተባባሉም ይመራረቃሉ፡፡ ካንተም በኋላ በልጅህ ይመራረቃሉ፡፡ በምትሔድበት መንገድ ሁሉ በረድኤት ጠብቄ ወደዚህ አገር እመልስሀለ” አለው፡፡ /ዘፍ.28፥13-ፍጻ/ 

ይህ አምላካዊ ቃል ኪዳን ከወላጅ ከዘመድ ተለይቶ የስደት ጉዞ ላይ ለነበረው ያዕቆብ ታላቅ ቃል ኪዳንና የምሥራች ነበር፡፡ በመሆኑም ያዕቆብ ይህንን ቃል ኪዳን ለሰጠው አምላክ ውለታውን እያሰበ ፍቅሩን ለመግለጽ ፈጣን ነበር፡፡ ያ ታላቅ ሕልም ያየበት ሌሊት ሲነጋ ተነሥቶ የእግዚአብሔር ስም ማስጠሪያ ይሆን ዘንድ ተንተርሶት ያደረውን ድንጋይ ወስዶ ሐውልት አድርጎ አቆመው፤ በላዩም ዘይት አፈሰሰበት፡፡ ስሙንም ቤቴል ብሎ ጠራው፤ ቤተ እግዚአብሔር ማለት ነው፡፡ በዚህም ብቻ አላበቃም፡፡ ስእለትም ተሳለ፡፡ “እግዚአብሔር በረድኤት ከኔ ጋራ ካለ በምሔድበትም ሀገር ሁሉ በረድኤት ከጠበቀኝ የዕለት ጉርስ ያመት ልብስ ከሰጠኝ ወደ አባቴም ቤት በደኅና ከመለሰኝ እግዚአብሔር ፈጣሪዬ ይሆንልኛል አለ፡፡ ፈጣሪውስ የግድ ፈጣሪው ነው እወደዋለሁ አመልከዋለሁ ሲል ነው፡፡ አንድም ይህን የሰጠኝ እግዚአብሔር አምላኬ ነው ማለት እሱን ብቻ አመልካለሁ ሌላ አላመልክም ማለት ነው፡፡ ይህችም የተከልኋት ደንጊያ የእግዚአብሔር ማደሪያ ትኾንልኛለች አለ፡፡ የሰጠኸኝን አሥራቱንም ሁሉ ላንተ ካሥር አንድ እሰጣለ“ አለ፡፡/ዘፍ.28፥20-ፍጻ/

በስደት በምንኖርበት ጊዜ እግዚአብሔር በተለያየ መንገድ የቸርነት ሥራውን ይሠራልናል፡፡ በበረከቱ ይጎበኘናል፡፡ በዚህ ጊዜ አባታችን ያዕቆብ እንዳደረገው ያንን ላደረገ እግዚአብሔር ውለታውን መክፈል ባይቻልም ፍቅራችንን በሥራ ለመግለጽ የተጋን መሆን አለብን፡፡ በያለንበት ክፍለ ሀገር ስሙ የሚቀደስበት መንግሥቱ የሚሰበክበት አብያተ ክርስቲያናት እንዲታነጹ ማድረግ፤ በተቋቋመበት ቦታ የምንኖር ከሆነም እንዲጠናከሩ ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡ እግዚአብሔር አብዝቶ ከሚሰጠን በረከትም አሥራት ማውጣት ይኖርብናል፡፡          

ለ. በስደት ሕይወት ትዕግሥት ማድረግ
አባቱ የመከረውን ምክርና የሰጠውን ትእዛዝ በመቀበል ያዕቆብ ወደ ሶርያ ሔዶ የሕይወት ጓደኛውን ራሔልን ቢያገኝም እንዳሰበው አገር አቋርጦ የመጣላትን የትዳር አጋሩን ይዞ ወደ አገሩ በቶሎ መመለስ አልቻለም፡፡ ይልቁንም አባቷ ላባ ባስቀመጠው ቅድመ ሁኔታ መሠረት ለሰባት ዓመታት የበግ ጠባቂው ሆኖ ሲያገለግል ቆይቷል፡፡ ከተሰደደ በኋላ አይቶ የወደዳትን ራሔልን በእጁ ያስገባ ዘንድ ሰባቱን ዓመት አገልጋይ ሆኖ የቆየው ያዕቆብ የተሰጠውን የጊዜ ገደብ ጨርሶ ልሂድ ብሎ ሲነሣ የራሔል አባት አልፈቀደለትም፡፡ ራሔልን ይዞ ለመሔድ ከፈለገ ሌላ ሰባት ዓመታትን እያገለገለ መቆየት እንዳለበት ነገረው፡፡ ያዕቆብ በተገባለት ቃል መሠረት ሰባት ዓመት ሲጠናቀቅ መሔድ ባለመቻሉ ቢያዝንም የመጣበት ዓላማ ግድ ይለዋልና ሌላ ሰባት ዓመታት ጨመረ፡፡ የእናቱ ፍቅር የወንድሙን የዔሳውን ብኲርናና ምርቃት መውሰድ እስኪያስችለው በፍቅርና በክብካቤ ያደገው ያዕቆብ ለ14 ዓመታት በግ ጠባቂ እረኛ ሆኖ በቀን ፀሐይና በሌሊት ቊር ሲሠቃይ ቢቆይም ተስፋ በመቁረጥ ተማሮ ወደ እናቱ አልሔደም፡፡ እርጅና ተጫጭኖት ሞት አፋፍ ላይ ሳለ ትቶት የመጣው አባቱ አሳስቦትና ናፍቆት ልሒድ አላለም ዓላማውን ማሳካት ነበረበትና በትዕግሥት ቆየ፡፡

ዛሬ በልዩ ልዩ ምክንያት በስደት የምንኖር ወገኖች ተወልደን ያደግንበ ትን ሀገርና ባሕል ትተን ስንመጣ ይነስም ይብዛ ይዘነው የመጣነው ዓላማ አለን፡፡ ይሁን እንጂ በስደት ሕይወት በሚያጋጥሙን ችግሮች የተነሣ ከዓላማችን የምናፈነግጥ ቁጥራችን ቀላል አይደለም፡፡ ብዙ ሰዎች እንደዚህ ዓይነት ችግር ውስጥ የሚገቡት በዋናነት በሁለት ምክንያት ነው፡፡ የመጀመሪያው ሲመጡ በአዕምሮአቸው ሥለውት የመጡት ነገርና ሲደርሱ የሚያጋጥማቸው የተለያየ መሆን ነው፡፡ ሲመጡ ውጭ አገር ገንዘብ በቀላሉ የሚታፈስ እንደሆነ አስበው ይመጡና ካሰቡት ቦታ ደርሰው ሲያዩት እንዳሰቡት ሳይሆን ሲቀር ይደናገጡና ከሀገራቸው የወጡበትን ቀን ይረግማሉ፡፡ ተስፋም ቆርጠው ሕይወታቸውን በአግባቡ መምራት ይሳናቸዋል፡፡

ነገር ግን ከአባታችን ከያዕቆብ የስደት ሕይወት የምንማረው ከዚህ የተለየ ነው፡፡ አባቱ ተነሥተህ ወደ ወገኔ ሒድና ሚስት የምትሆንህን ይዘህ ና ሲለው ምናልባት በወጣትነት አእምሮው እንደ ደረሰ በዓይኑ ዐይቶ የፈቀዳትንና የወደዳትን ይዞ እንደሚመለስ አስቦ ይሆናል፡፡ ነገር ግን ሶርያ ሲደርስ ያጋጠመው ሌላ ነገር ነው፤ የ14 ዓመታት የእረኝነት ሕይወት፡፡ ይሁን እንጂ በዚያ ደንግጦ ወይም ተበሳጭቶ ወደ አገሬ ልመለስ አላለም፡፡ በዚያው ሲቆይም ዕለት ዕለት ሲበሳጭና ተስፋ ሲቆርጥ እንደነበረ መጽሐፍ አያስነብበንም፡፡ ስለዚህ በስደት ሕይወት ስንኖር ባልጠበቅነው ሁኔታ በሚያጋጥመን ችግር የተነሣ ሳንሳቀቅ ከሀገራችን ስንወጣ ይዘነው የወጣነውን ዓላማ አጽንተን ለስኬታማነቱ እየታገልን ልንኖር ያስፈልጋል፡፡ ያንን ያደረግን እንደሆነ ያዕቆብ ራሔልን ከነአገልጋዮቿ ይዞ አገሩ እንደገባ እኛም በዕውቀት በልጥገን በገንዘብ ከብረን አገራችን እንገባለን፡፡

ሌላው ምክንያት የወጡበትን ዓላማ በአግባቡ ለመረዳት አለመቻል ነው፡፡ ብዙ ጊዜ ሰዎች ወደ ውጭ የሚወጡት በተረዳ ነገር ሰፍረው ቆጥረው በዕቅድ ያወጡትን ዓላማ ሳይዙ ነው፡፡ ያ ባለመሆኑም በስደት ሕይወታ ቸው በሚያጋጥማቸው ችግር በቀላሉ መደናገጥና መማረር ብሎም ተስፋ መቁረጥ ያጋጥማቸዋል፡፡ በስደት ሕይወት ይቅርና በየትኛውም ሕይወቱ ቢሆን ሰው የሚመራበት የሕይወት ዓላማ ያስፈልገዋል፡፡ ዓላማ የሌለውና ዓለማውን በአግባቡ ያለተረዳ ሰው በየመንገዱ በሚፈጠሩ ችግሮች /መሰና ክሎች/ በቀላሉ ለመውደቅ የተመቻቸ ይሆናል፡፡ ዓላማ ያለውና በአግባቡ ዓላማውን የተረዳ ሰው ግን በጥንካሬ የሚጓዝ፣ በቀላሉ የማይወድቅና ቢወድቅም ፈጥኖ የሚነሣ ሰው ነው፡፡ አባታችን ያዕቆብ ከሀገሩ የወጣበትን ዓላማ ያልተረዳ ቢሆን ኖሮ በፍጹም አስቦትና ሆኖት የማያውቀውን ሕይወት ለ14 ዓመታት ይቅርና ለ4 ቀናትም ቢሆን ታግሦ ሊቆይ አይችልም ነበር፡፡  

    
ሐ. ያሰቡትን ካገኙ በኋላ ወደ ተወለዱበት ሀገር መመለስ
ያዕቆብ ከ21 ዓመታት አገልግ ሎት በኋላ ራሔልን ሲያገኝ ራሔልንና በስደት ያጠራቀመውን ሀብት ይዞ ወደ ተወለደበት ሀገር ሊመለስ ወሰነ፡፡ ዓላማውን ካሳካ በኋላ በባዕድ ምድር ተጨማሪ ዓመታትን በባዕድነት መቆ የት አልፈለገም፡፡ ፈጣሪው እግዚአ ብሔርም ተመለስ አለው፡፡ /ዘፍ.31፥3/ እሱም ተመለሰ፡፡

ሰዎች በስደት ሕይወት ሲኖሩ ከሀገር ይዘውት የሚመጡት ግልጽና የጸና ዓላማ ሊኖር እንደሚገባ ሁሉ ዓላማቸውን ከግብ ካደረሱ በኋላ ሊኖር ስለሚገባው ሕይወት ማሰብ አግባብ ነው፡፡ በተለያዩ ቦታዎች ከሀገራቸው ከወጡ በኋላ ረጅም ጊዜ በስደት የኖሩ ሰዎች ዓላማቸውን ካሳኩ በኋላም ወደ ሀገራቸው ለመመለስ የማያስቡ ይኖራሉ፡፡ በእርግጥ ከእነዚህ ውስጥ ወደ ሀገራቸው እንዳይገቡ የሚያደርጓቸው በቂ ምክንያቶች የሚኖሯቸውም አይጠፉም፡፡

ዓላማን ከግብ ካደረሱ በኋላ ወደ ሀገር መመለሱ ለተመላሹ ከሚሰጠው የአእምሮ ዕረፍትና የተረጋጋ ሕይወት ባሻገር ከተመላሹ በሚገኘው ዕውቀት፣ ልምድ፣ ሀብትና ጥረት ወገንና ሀገር እንዲጠቀም ያስችላል፡፡ ያዕቆብ ዓላማውን ካሳካ በኋላ በመመለሱ ሕዝበ /ሀገረ/ እስራኤልን በአዕማድነት የመሠረቱ ልጆች ለማፍራት ችሏል፡፡

በዚህም ዘመን ሰፊ ራእይ ሰንቀን ሩቅ አልመን ወደተለያዩ ሀገሮች የተሰደድን ኢትዮጵያውያን በከፈልነው መሥዋዕትነትና በእግዚአብሔር አጋዥነት ዓላማችን ከተሳካልን በኋላ ወደ ሀገራችን ልንመለስ ያስፈልጋል፡፡ “ሠናይ ለብእሲ ለእመ ይከውን መቅበርቱ ውስተ ርስቱ፤ የሰው ሞቱ፤ መቃብሩም በሀገሩ /ርስቱ/ ቢሆን መልካም ነው“ እንደተባለ መመለስ የማያስችለን መሠረታዊ ችግር ከሌለ በስተቀር የተሰደድንበት ዓላማ ከተሳካ በኋላ በባዕድ ምድር ውሎ ከማደር ይልቅ ባካበትነው ቁሳዊና አእምሮአዊ ሀብት ሀገርንና ወገንን በመጥቀም ለመጠቀም ቤተሰብን ይዞ፤ ሀብትንም ሸክፎ ርስት ሆና ወደ ተሰጠችን ምድረ ኢትዮጵያ ለመግባት ማመንታት የለብንም፡፡ ያዕቆብን ተመለስ ብሎ ያዘዘው እግዚአብሔር ፈጣሪያችን ወደሀገራችን እንድንመለስ ፈቃዱ እንደሆነም እንረዳለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት 16 ከግንቦት 1-15 ቀን 2005 ዓ.ም.