ለማእከላት ጸሐፊዎችና ለማስተባበሪያ ሓላፊዎች ሥልጠና ተሰጠ

ሰኔ 13 ቀን 2005 ዓ.ም.

ታመነ ተ/ዮሐንስ

ሰኔ 1 እና 2 ቀን 2005 ዓ.ም በማኅበሩ ሥራ አመራርና አስፈጻሚ አካላት አወያይነት የማእከላት መደበኛ ጸሐፊዎች፣ መደበኛ መምህራንና የስድስቱ ማእከላት የማስተባበሪያ ጽ/ቤት ሓላፊዎችን ያሳተፈ ሥልጠናና ውይይት ተካሔደ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን የሀገር ውስጥ ማእከላትና ግቢ ጉባኤያት ማደራጃና ማስተባበሪያ ዋና ሓላፊ የሆኑት ዲ/ን አንዱአምላክ ይበልጣል በስልጠናው መክፈቻ መርሐ ግብር ላይ በሰጡት ማብራሪያ ተሳታፊዎቹ ለማኅበሩ አገልግሎት ከፍተኛ ድርሻ ያላቸው በመሆናቸው በማኅበሩ የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ፕላን ዙሪያ ማወያየት ለአገልግሎቱ መቃናት አጋዥ የሆነ ሥልጠና መስጠት ተገቢ ሆኖ እንደተገኘ ገልጸዋል፡፡

በዚህም መሠረት በሙያው ልምድ ባላቸውና የማኅበሩ የልማት ተቋማት አስተዳደር ቦርድ አባል በሆኑት በአቶ መንክር ግርማ “Communication & team development” በሚል ርዕስ ሥልጠና የተሰጠ ሲሆን አባላቱ በቀጣይ የአገልግሎት ቆይታቸው ችግሮችን በምን ዓይነት ሁኔታ መፍታት እንዳለባቸው ግንዛቤ እንዲያገኙ ተደርጓል፡፡

በተጨማሪም ማኅበሩ ያለበትን ነባራዊ ሁኔታ ማእከላቱ እንዲረዱ በማድረግ በዋነኝነት ያለባቸው የሥራ ሓላፊነት የስብከተ ወንጌል ማስፋፋትና ማጎልበት ስለሆነ ሰፊውን ጊዜ በስብከተ ወንጌል አገልግሎቱ ላይ ያሉ ችግሮችና መፍትሔዎቻቸው ዙሪያ ውይይትና የልምድ ልውውጥ ተካሒዷል፡፡  

 
በስልጠናው ላይ ከስድስቱ ማስተባበሪያ ማእከላት ሠላሳ አምስት ተሳታፊዎች ተገኝተዋል፡፡

 

ዕርገት(ለሕፃናት)

ሰኔ 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

በአብርሃም ቸርነት/ዘገዳመ ኢየሱስ/

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ በተነሣ በአርባኛው ቀን ቅዱሳን ሐዋርያት በጸሎት ይተጉ ወደነበረበት ቤት በመሄድ ደቀመዛሙርቱን ይዟቸው ከቤት በመውጣት መንገድ ጀመረ፡፡ እርሱ ከፊት ከፊት እየመራቸው እነርሱ እየተከተሉት ወደ ረጅሙና በረጃጅም ዛፎች ወደ ተሞወው ደብረ ዘይት ተራራ ይዟቸው ወጣ፡፡

በተራራው ጫፍ /አናት/ ላይ ሲደርሱ፤ በመካከላቸው ቆሞ ሐዋርያትን እንዲህ ብሎ መከራቸው “ከእኔ የተማራችሁትን ትምህርት ጠብቁ በቤተ ክርስቲያንም ጸንታችሁ ኀይልን ከሰማይ እስክልክላችሁ ቆዩ” ብሎ አዘዛቸው፡፡ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ አሥራ ሁለቱን ሐዋርያት እጁን በላያቸው ጭኖ (በአንብሮተ ዕድ) ሾማቸው፡፡

ይህንንም እየነገራቸው ከምድር ወደ ሰማይ ከፍ፣ ከፍ፣ ከፍ አለ፡፡ ነጭ የሆነችና ለዓይን በጣም የምታምር ብሩህ ደመናም አምላካችንን ተቀበለችው፡፡ ከዓይናቸውም እየራቀ፣ እየራቀ፣ ከእይታቸው ተሰወረባቸው፡፡
ሐዋርያትም ኢየሱስ ክርስቶስን በጣም ይወዱት ስለነበረ ሲለያቸው አዝነው አተኩረው ሰማይ ሰማዩን ለረጅም ሰዓት ተመለከቱ፡፡ ድንገትም ነጫጭ ልብስ የለበሱ ሁለት ቅዱሳን መላእክት በአጠገባቸው ቆመው ታዩአቸው፡፡ መላእክቱም ሐዋርያትን እንዲህ አሏቸው፡፡ “እናንተ የገሊላ ሰዎች ሆይ ወደ ሰማይ እያያችሁ ለምን አዝናችሁ ቆማችሁ፡፡ ይህ ከእናንተ ወደ ሰማይ ያረገው ኢየሱስ ከእናንተ ወደ ሰማይ ሲያርግ እንዳያችሁት እንዲሁ ዳግመኛ ወደ ምድር ይመጣል፡፡” አሏቸው፡፡

ሐዋርያቱም የመላእክቱን ማረጋጊያ ቃል ከሰሙ በኋላ ፈጥነው በኢየሩሳሌም ወደምትገኘው ቤተ መቅደስ በመሄድ እግዚአብሔር ቃል የገባላቸውን ኀይል ከሰማይ እንዲልክላቸው ቀን ከሌሊት በአንድነት ሆነው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምንም ከመካከላቸው አድርገው በጸሎት እየተጉ ቆዩ፡፡
ጥቅስ፡- ሉቃ.24፥50-53፣ ሐዋ.1፥9-14

በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚታየውን የአሠራር ብልሹነት ማሰወገድ እንደሚገባ ተገለጸ

ሰኔ 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

በትዕግሥት ታፈረ

በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ውስጥ የሚታየውን የአሠራር ብልሹነት ማሰወገድ እንደሚገባ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖትና ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ገለጹ፡፡

ቅዱስነታቸው ይህንን የገለጹት በግንቦቱ ርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ባስተላለፈው ውሳኔ መሠረት የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፤ እንዲሁም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው የተመረጡት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ሓላፊዎችና ሠራተኞች ጋር ሰኔ 4 ቀን 2005 ዓ.ም. የትውውቅ መርሐ ግብር በተካሄደበት ወቅት ነው፡፡

የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሆነው የተመረጡት ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የወላይታና ዳውሮ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በትውውቅ መርሐ ግብሩ ላይ ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል የሁሉም እገዛ እንደሚያስፈልግ የገለጹ ሲሆን “ለቤተ ክርስቲያናችን ተልእኮ ከተመረጥንና እንድናገለግል ከተጠራን አገልግሎታችን የተሻለ መሆን አለበት፡፡ የሚያዘን ሥርዓታችን፤ ፍቅራችንና ሕጋችን እንጂ ሥልጣናችን ሊሆን አይገባም፡፡ ሥልጣናችን የሚያዘን ከሆነ ሥራችን ሙሉ ሊሆን አይችልም፡፡ ትክክለኛ መሪን ማንም አይጠላም፤ መሪዎችን ተመሪዎች የሚጠሏቸው ከቆሙለት ዓላማና ተግባር ውጪ በአምባገነንነት፤ በጉቦኝነት፤ በዘረኝነት፤ በአድሏዊነት ሱስ ሲጠመዱ ተመሪዎች ያኮርፋሉ፤ ይጨነቃሉ፤ ማንንም ስለማያምኑ እንደ ቃየል ጥላቸው ያስደነግጣቸዋል፡፡  ስለዚህ ሀሰትን የምትጠየፉ፤ አሉባልታን የምትንቁ፤ ሥራን የምትወዱ፤ ሰላምን የምትናፍቁ፤ ፍቅር የምትላበሱ መሆን አለባችሁ፡፡ ወደፊት አብረን ስለምንጓዝ  እግዚአብሔር እንዲረዳን ቅድሰት ቤተ ክርስቲያናችንን አሳድገን እኛም ተረድተን ሌሎችን እንድንረዳ ያስፈልጋል” ብለዋል፡፡

በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የቅዱስ ሲኖዶስ ጸሓፊ ሆነው የተመረጡት ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በበኩላቸው ባደረጉት ንግግር “መሰባሰባችን መልካም ነው፡፡ ሁላችንም ግዴታችንን ከተወጣን ያለው ችግር ይወገዳል፡፡ በእውነተኞች ሰዎች ቸርነትና በጎነት አገር ትቀናለች፡፡ አገር ስትቀና ሰው ሁሉ በሰላም ይኖራል፡፡በኅብረት ሆነን ዘመኑን በመዋጀትና በመገምገም በትክክል ሥራችንን ከሠራን ይቃናልናል፡፡” በማለት ተናግረዋል፡፡

የጠቅላይ ቤተ ክህነት አስተዳደርና ሠራተኞች እንዲሁም የተለያዩ የቤተ ክርስቲያኒቱ አካላት ሠራተኞች ችግሮች ናቸው ያሏቸውን አሳቦች ያቀረቡ ሲሆን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ወጥ የሆነ የአሠራር ዘዴ ያለመኖር፤ አለቆች በተለዋወጡ ቁጥር በሚመጣው ሰው ላይ ሠራተኛው ለመንጠልጠል የራሱን ዘዴ መቀየስ፤ በአሠራር ሥርዓቱ ሁሉም ሠራተኛ እኩል መመራት ያለመቻል፤ ሹማምንትን በመፍራት፤ በመስገድና በመሽቆጥቆጥ አማላጅ በመላክ የተሻለ ሥራ ለማግኘት ጥረት ማድረግ፤ ወዘተ. . . የሚሉት በሠራተኞቹ የተጠቀሱ ሲሆን ይህ አካሄድ በአስተዳደርና በስብከተ ወንጌል ተልእኮ ስኬታማ ጉዞ ላይ አሉታዊ ተጽእኖ እንደሚፈጥር በመግለጽ የአሠራር ዘዴ /System/ መዘርጋት እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት በሰጡት ቃለ ምእዳን “ቤተ ክርስቲያናችን ከጥንታዊያንና ከታሪካዊያን የዓለም አብያተ ክርስቲያናት አንዷና አንጋፋዋ መሆኗ የተረጋገጠላት ናት፡፡ ይህ ሊሆን የቻለው አባቶቻችን ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፤ ከሐዋርያትና  ከሊቃውንቱ ተረክበው ሕልውናዋንና ክብሯን ጠብቀው ስላስተላለፉልን ነው፡፡ እኛም ለሚቀጥለው ትውልድ ለማስተላለፍ ትልቅ ሓላፊነት ይጠብቀናል፡፡ ስለዚህ ጥንተ ቅድስናዋን፤ ንጽሕናዋንና ታሪኳን መመለስ አለብን፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በሃይማኖት እንከን የላትም፡፡ በአሁኑ ወቅት በአስተዳደር ጤነኛ አይደለችም፤ ብዙ ብልሹነት ይታያል፡፡ ለቤተ ክርስቲያናችን የማይስማሙ ነገሮች ወደ ቤተ ክርስቲያናችን ገብተው መንገዳችንን እያበላሹብን ነው፡፡ ሙስና፤ ዘረኝነትና ሌሎችም ክፉ ነገሮች ይታያሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን የመልካም ሥራ መሪ እንድትሆን እንፈልጋለን፡፡ አስተማሪ እንጂ ተማሪ መሆን የለባትም፡፡ ሓላፊነት፤ ተጠያቂነት፤ እውነተኛነት፤ ሃቀኝነትና የሕግ የበላይነት የሰፈነባት መሆን ይገባታል፡፡” ብለዋል፡፡

ሰዋስወ ግእዝ

ሰኔ 13 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ት ኑኀሚን ዋቅጅራ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

በቅድሚያ በሕያውና ዘለዓለማዊ በሆነ በእግዚአብሔር ስም የከበረ ሰላምታዬን እያቀረብኩ ስለ ግእዝ ቋንቋ አጠር ባለ መልኩ እገልጻለሁ፡፡

የግእዝ ቋንቋ ቀዳማዊነት

ቋንቋ ማለት መግባቢያ መተዋወቂያ መነጋገሪያ አሳብ ለአሳብ መገላለጫ ወዘተ…… ማለት ነው፡፡ ሕዝብ ባለበት ቦታ ሁሉ ቋንቋ አለ፤ ቋንቋም ባለበት ቦታ ሕዝብ አለ፤ ያለ ሕዝብ ቋንቋ ያለ ቋንቋ ሕዝብ ሊኖር አይችልም፡፡ ይህን መነሻ በማድረግ ስለ ግእዝ ቋንቋ አመጣጥ አጠር ባለ መልኩ ስንነጋገር፡-

ከአንዳንድ ቀደምት የታሪክ ጸሐፊዎችና የግእዝ ቋንቋ መጻሕፍትን ጽፈው ካስረከቡን ቀደምት የቤተ ክርስቲያን አባቶችና የቋንቋው ባለቤቶች እንደምንረዳው፡- የግእዝ ቋንቋ አመጣጥ በኢትዮጵያ መነሻ ሊሆነን የሚችለው ከስምንተኛው ምዕተ ዓመት ቅድመ ልደት ክርስቶስ ጀምሮ ነገደ ሴም /የሴም ዘሮች/ወገኖች/ ቋንቋቸውን ይዘው ወደ ኢትዮጵያ ከመጡበት ጊዜ ጀምሮ ሴማዊ ቋንቋ በኢትዮጵያ ሀገራዊ ቋንቋ ሆነ፡፡ ነገደ ሴም ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣታቸው በፊት ቋንቋቸውን በመግባቢያነት አሳድገው፣ ሥነ ጽሑፋቸውን አስፋፍተው፣ በባቢሎን በአካድና፣ በአሶር ይኖሩ ነበር፡፡ በኋላ ግን ለሁለት ተከፍለው ግማሾቹ ሴማውያን ሰሜንና ምስራቅ እስያን፣ ግማሾቹ ሴማውያን ደግሞ ደቡቡ እስያን ይዘው ይኖሩ ነበር፡፡

የሰሜን እስያ ሴማውያን ቋንቋ /የአካድ ቋንቋ/ አማራይክ፣ ዕብራይስጥንና ፊንቄን ሲያስገኝ የደቡብ እስያ ሴማውያን ቋንቋም /አካድ ቋንቋ/ ሳባን ግእዝንና የተለያዩ በኢትዮጵያ ውስጥ በመግባቢያነት የምንጠቀምባቸውን ሴማውያን ቋንቋዎች አስግኝቷል፡፡ በደቡብ እስያ ይኖሩ የነበሩ ነገደ ሴም በተለያየ ምክንያት እየፈለሱ ወደ ደቡብ ዐረብ፣ ወደ የመንና ወደ አካባቢዋ መጥተዋል ከዝያም ፈልሰው ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት በአክሱምና በአካባቢዋ ሰፍረው ይዘዋቸው ከመጡት ቋንቋዎቻቸው መካከል በታሪክ ጎልተው የሚታወቁና አገልግሎት ሲሰጡ የነበሩትና በአሁኑ ሰዓትም በአገልግሎት ላይ የሚገኙት ቋንቋዎች የሳባ እና የግእዝ ቋንቋዎች ናቸው፡፡

ነገደ ሴም /ሴማውያን/ ቋንቋዎቻቸውን /ሳባና ግእዝን/ ከነገደ ካም ቋንቋ ጋር አስማምተው በመያዝ ሁሉንም ቋንቋዎች ሲናገሩዋቸው ኖረው ነበር፡፡ በኋላ ግን ሳባና ግእዝ እየተለመዱና እየተስፋፉ እየዳበሩም ከመሄዳቸው የተነሣ የነገደ ካምን ቋንቋ እየዋጡት መጥተው ሁለቱ ሳባ እና ግእዝ ቋንቋዎች ብቻ ሀገራዊ ቋንቋዎች ይሆኑ ጀመር እየቆዩ ግን ሁለቱ /ሳባና ግእዝ/ በጣም ተመሳሳይና ተቀራራቢ በመሆናቸው እንደ አንድ ቋንቋ ሆነው ይነገሩ ጀመር፡፡ ይኸም ጽሑፉ /ፊደሉ/ በሳባ እንዲጻፍ እና መነጋገሪያ ቋንቋውን ደግሞ በግእዝ እንዲሆን በመደረጉ ነው፡፡ ነገደ ሴም በሳባ ቋንቋቸው ሳባውያን፣ በግእዝ ቋንቋቸው ደግሞ አግአዝያን ተብለው የሚጠሩት ከዚህ መነሻነት ነበር፡፡

ለዚህም መረጃ የሚሆኑን ሳባና ግእዝ ቋንቋዎች ተጽፈውባቸው የሚገኙት ጥንታውያን የኢትዮጵያ ቅርሶች እንደ የአክሱምና የላሊበላ ሐውልቶች በየሐ እና በአዱልስ ወዘተ….. የተለያዩ በድንጋይ ላይ የተቀረጹ ጽሑፎችና ቅርጻ ቅርጾች እስከ አሁን ቆመው የሚገኙ የዚህ ቋሚና ግልጽ ማስረጃዎች ናቸው፡፡ የሳባና የግእዝ ቋንቋዎች በዚህ ሁኔታ እስከ 324 /፫፻፳ወ፬/ዓ.ም. አካባቢ ድረስ አብረው ሲነገሩ ቆይተዋል በኋላ ግን የሳባ ንቋ እየተዳከመና በግእዝ ቋንቋ እየተዋጠ ይሄድ ጀመር እንደ ምንም እየተንገዳገደ እስከ 350 /፫፻፶/ ዓ.ም. ቆይቶ ከዚህ በኋላ ከሥነ – ጽሑፍ ከመነጋገሪያነትም ፈጽሞ ቀረ የግእዝ ቋንቋ ግን ከ324 /፫፻፳ወ፬/ዓ.ም. ጀምሮ ብቸኛ ሀገራዊ ቋንቋ በመሆን እስከ ፲፪ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ማለትም የአማርኛ ቋንቋ ብሔራዊ ቋንቋ ሆኖ ሲያገለግል እንደ ነበር የታሪክ ጸሐፊዎች በግልጽ አስቀምጠውታል፡፡
፩.፪. የግእዝ ፊደላት አመጣጥ

ስለ ግእዝ ቋንቋ ስንነጋገር በመጀመሪያ ለማንኛውም ቋንቋ መሠረት ስለሚሆነው ስለ ፊደል አመጣጥ ማወቅ ተገቢ ነው፡፡ ስለ ፊደል አመጣጥ ሊቃውንት ብዙ ትንታኔ ይሰጡበታል ይኸውም ፊደል ማለት ጽሑፍ ነው ምክንያቱም “ፈደለ” ጻፈ ከሚለው ከግእዝ ቃል የወጣ ነው ይላሉ፡፡ ይሁን እንጂ “ፈደለ” የሚለውም ቃል የሦስት ፊደላት ጥምረት በመሆኑ እነዚህ ፊደላት ከየት እንደመጡ መነሻቸውን /ምንጫቸውን/ ማወቅ ተገቢ ነው፡፡

እንደ ቤተ ክርስቲያናችን ትምህርት ለዚህ በቂ የሆነ መረጃ እናገኛለን፡፡ የፊደል ስልት አንድም ቅርጽ የተጀመረው የአዳም ሦስተኛ ትውልድ በሆነው በነቢዩ በሄኖስ ዘመን ነው፡፡ ነቢዩ እግዚአብሔርን በማገልገል የታወቀ ደግ ስለ ነበር ለደግነቱ መታወቂያ /መታሰቢያ/ ይሆነው ዘንድ በእግዚአብሔር ፈቃድ የሕግ ማሰሪያ የሚሆነውን ፊደል በጸፍጸፈ ሰማይ /በሰማይ ገበታነት/ ተገልጦ ታይቶታል፡፡

ስለዚህ የፊደል ቅርጽ ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ለሥነ-ጽሑፍ በር መክፈቻ በማድረግ ተጠቅመውበታል፡፡ መጠሪያ ስሙንም ጽሑፍ ለማለት ፊደል ብለውታል፡፡ ይኸስ እውነትነቱ ምን ያህል ያገለግላል ቢሉ በዚያን ጊዜም በጸፍጸፍ ሰማይ ታየ የሚባለው ፊደል የእብራይስጥ ፊደል እኛ አሁን አሌፉት እያልን የምንጠራው ነው፡፡

ስለዚህ ይህ ፊደል ከፊደልነት ጥቅሙ ጋር እንደ ኅቡዕ ስም ይገመታል /ይታመናል/ ምክንያቱም የእያንዳንዱ ፊደል ትርጒም ከእግዚአብሔር ህልውና እና እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ካደረጋቸው የቸርነት ሥራዎች ጋር የተዛመደ ትርጒም ስለሚሰጥ (ስለአለው) ነው፡፡ ይህ እውነታ እና የስም አጠራር ትርጒም ግን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሊቃውንት አባቶች የፊደላት ትርጒም አሰጣጥ ላይ በግልጽ ተጽፎ የሚገኝ ነው /ጥንታዊ የኢትዮጵያ ትምህርት በሊቀ ሥልጣናት ሀብተ ማርያም ወርቅነህ/ በተጻፈው መጽሐፍ በግልጽ እንረዳዋለን ይህን መነሻ በማድረግ የሥነ-ጽሑፋችን በር መክፈቻ የአሌፋቶችን ስም ፊደል የሚል ስያሜ በመስጠት እንጠቀምበታለን፡- ስለዚህ ማንኛውንም ነገር ለመጻፍ ለመጪውም ትውልድ ለማስተላለፍ በጽሑፍ መቀረጽ ስላለበትና ራሱ ፊደሉ የሥነ-ጽሑፍ መጀመሪያ ስለሆነ ጽሑፍ ለማለት ፊደል ተብሎ ተጠርቷል፡፡

ለዚህም የቤተ ክርስቲያን  አባቶች ሊቃውንት አጽንዖት ሰጥተው ሲያስቀምጡት “ዘእንበለ ፊደል ኢይትነገር ወንጌል” ይላሉ ይህ ማለት ወንጌል ሳይቀር የሚጻፈው /የሚተረጎመው/ በፊደል አማካኝነት ነው፡፡ ከዚህም ሌላ ስለ ፈደል ጠቃሚነት የሚሰጡትን ሐተታዎች ከብዙ በጥቂቱ እንመልከት፡-

፩. ፊደል- ብሒል ነቅዓ ጥበብ ውእቱ፡፡

ፊደል የአእምሮ መገመቻ የምሥጢር መመልከቻ ነው ምክንያቱም ያለ ፊደል ምንም አይታወቅምና ፡፡

፪. ፊደል – ብሂል ነቅዓ ጥበብ ውእቱ፡፡

ፊደል የጥበብ ሁሉ መገኛ ምንጭ ነው፡፡

፫. ፊደል – ብሂል መራሔ ዕውር ውእቱ፡፡

ፊደል የእውር መሪ ነው፤ ምክንያቱም ሰውን ሁሉ ከድንቂርና አውጥቶ ወደ ብርሃን ይመራልና፡፡

፬. ፊደል – ብሂል ጸያሔ ፍኖት ውእቱ፡፡

ፊደል ማለት መንገድ ጠራጊ ነው፤ ምክንያቱም አላዋቂነትን /ድንቁርናን/ ከሰው ልጅ ጠርጎ /አጽድቶ/ ከፍጹም ዕውቀት ያደርሳልና፡፡

፭. ፊደል ብሂል -ርእሰ መጻሕፍት ውእቱ፡፡

ፊደል ማለት የመጻሕፍት ሁሉ ራስ /አናት/ ነው ምክንያቱም ያለ ፊደል ምንም ነገር መጻፍ አይቻልምና፤ /ኢተወልደ መጽሐፍ ዘእንበሌሁ ለፊደል/ ያለ ፊደል ምንም ነገር ሊጻፍ አይቻልምና

የግእዝ ቋንቋ ከሴማውያን ፊደሎች መካከል አንዱና ዋናው ጥንታዊ ቋንቋ ስለሆነ፣ የራሱ የሆነ ብዙ ቃላትን ከነፍቺዎቻቸው ይዞ ይገኛል፡፡ ከዚህ አንጻር ፊደል የማንኛውም ጽሑፍ መነሻ ስለሆነ፣ ጽሑፍ ብሎ ለመጥራት መጠሪያውን ፊደል ብለውታል፡፡ በአጠቃላይ ቋንቋ እንደ ማንኛውም ቋንቋ የራሱ የሆነ የአጻጻፍን ሥልትና ቅርጽ የተከተለ ጥንታዊና መሠረታዊ ቋንቋ ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

ይቆየን

የቅዱስ ፓትርያርኩ መልእክት ቤተ ክርስቲያኒቱ በአንገብጋቢነት የምትሻውን ወቅታዊ ጥያቄ የሚመልስ አሳብ የያዘ ነው

 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ

 
ከአራት ዓመት በፊት 2001 ዓ.ም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደ ተሻለ የአገልግሎት ደረጃ ለማድረስ በመከረበት ጉባኤው ቤተ ክርስቲያኒቱ ያሉባትን ለአገልግሎቱ እንቅፋት የሆኑ ተገቢ ያልሆኑ ድርጊቶችን ለማስወገድ ያሳለፋቸው ውሳኔዎች፣ የተያዙ አቋሞች ነበሩ፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ በጊዜው በቤተ ክርስቲያኒቱ “የአስተዳደር ችግሮች፣ የሙስናና የቤተሰብ አስተዳደር” በቤተ ክርስቲያኒቱ የአገልግሎት መስመሮች ውስጥ ሁሉ መንሰራፋቱን አምኖ ያንን ለማጥራት፣ ዘመኑን የዋጀ በተጠና ዕቅድና አፈጻጸም የሚከናወን፣ ሓላፊነትና ተጠያቂነት የሰፈነበት ዘመናዊ የአስተዳደር ሥርዓት ለመዘርጋት ውሳኔ ማስተላለፉ የሚታወስ ነው፡፡ 

ይሁን እንጂ ወደ ተግባር ለመግባት የተደረገው እንቅስቃሴ ግን ወዲያውኑ ፈተና ገጥሞት ነበር፡፡ ውዥንብር ለመፍጠር፣ አለመግባባትን ለማስፈን የአባቶችን ስም በማጥፋት ለማሸማቀቅ በተለያዩ መንገዶች ጥረት የሚያደርጉ፣ በተናጠልና በቡድን የሚን ቀሳቀሱ የተለያዩ አካላት ስለነበሩ ርምጃው ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ በመሠረተ አሳቡ ግን የቤተ ክርስቲያኒቱን የአገልግሎት አካሄድ የማሳደግና የሚያስወቅሱ ነገሮችን የማስወገድ ብርቱ ፍላጎት እንደነበረው ቅዱስ ሲኖዶስ በአቋሙ አሳይቶ አልፏል፡፡

ይህ የነበረ የቅዱስ ሲኖዶስ ሐሳብ ዛሬ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በግልጽ የተግባራቸው መጀመሪያ፣ የትኩረት አቅጣጫዎቻቸው ሁሉ ራስ እንደሆነ በቅርቡ ለበዓለ ትንሣኤ ባስተላለፉት ይፋዊ መልእክትና ለእንኳን አደረሰዎ በተዘጋጀው መርሐ ግብር ላይ  ባንጸባረቁት አቋም ከላይ አስቀድመን ያነሣናቸውን የቅዱስ ሲኖዶስ አቋሞች አስተጋብተዋል፡፡ ሃይማኖት በምግባር መገለጽ እንዳለበትና ከሃይማኖቱ አሳብ ጋር ስምሙ የሆነ አካሄድ እንዲኖረን የመከሩት ቅዱስነታቸው “ያረጀው ነገር ሁሉ በክርስቶስ ደም ተቀድሶና ነጽቶ ሐዲስ ሆኗል፡፡ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሠርቶ የሚያሠራ የመልካም ነገር ሁሉ አርአያ መሪ እንደመሆኑ መጠን አዲሱን መንገድ ከፍቶ እንድንጓዝበት ሲያደርግ እኛም በአዲስ መንፈስ በአዲስ ሕይወት ልንመላለስበት እንጂ እንደገና ወደ አረጀውና ወደ አፈጀው ሕይወት ተመልሰን ልንዘፈቅ አይደለም” ብለዋል፡፡

መልእክታቸው የቤተ ክርስቲያን ልጆችና አገልጋዮች ሁሉ በየደረጃው ያሉ ፍጹም ክርስቲያናዊ ምግባር እንዲላበሱ ያላቸውን አባታዊ ፍላጎት አንጸባርቀዋል፡፡ ይህ የቅዱስነታቸው ምክር በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር አካላትም ዘንድ ሊተኮርበት የሚገባ ነው፡፡ ለመልካም ምግባር እንድንሰለፍ በሥራችንም ሁሉ እንድንበረታ ባስተላለፉት በዚሁ ምክራቸው መሠረት የትኞቹም አገልጋዮች መመላለስ ቢችሉ ቤተ ክርስቲያን አሉባት ከሚባሉ ችግሮች ሁሉ መላቀቅ የሚያስችላት አቅም ይሆናል፡፡

ቅዱስነታቸው በተለይም በዕለተ ማዕዶት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቤተ ክህነቱ ከፍተኛ የሥራ ሓላፊዎች፣ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች በተገኙበት ባስተላለፉት መልእክት በዓሉ ከዲያብሎስ ቁራኛነት ከሞት አገዛዝ ከአሮጌው እርሾ የተላቀቅንበት መሆኑን ካወሱ በኋላ በዚያው አንጻር የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ከብልሹ አስተሳሰብ፣ ከብልሹ ምግባር ከሙስና፣ ከብልሹ አሠራር መጽዳት እንደሚገባቸው አሳስበዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ያላትን ቅድስና ጠብቃ እንድትኖር ልጆቿ በተለይም አርአያ ሊሆኑ የሚገባቸው ካህናት በጎ ካልሆኑና ቤተ ክርስቲያንን ከሚያስተቹ አስተሳሰብና ተግባር እንዲላቀቁ መክረዋል፡፡ ይህም ቀድሞም የነበረው የቅዱስ ሲኖዶስ ቀርጥ አሳብ ተግባራዊ ምላሽ ሊያገኝ የሚችልበት ዕድል እንዳለ ተስፋ ሰጪ ሆኗል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የቅዱስነታቸው መልእክት ተገቢና ወቅታዊ መሆኑን የሚያምን ሲሆን ለቤተ ክርስቲያኒቱ አገልግሎት ዕድገት በቀና መንፈስ ለሚያስቡ የቅዱስነታቸው የአገልግሎት ጅማሬ ተስፋ ሰጪ እንደሆነ ያስባል፡፡ ይህ የቅዱስነታቸው አቋም በዚሁ ወቅት በሚካሄደው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ብርቱ ድጋፍ እንደሚያገኝና ጠንከር ያሉ መመሪያዎችን በየደረጃው ላሉ የቤተ ክህነቱ አገልጋዮች ያስተላልፋል ተብሎ ይታመናል፡፡

ከሁሉም በላይ ግን የቅዱስነታቸው መልእክትም ሆነ የቅዱስ ሲኖዶስ አቋም በየደረጃው ባሉ አካላት ተግባራዊ ምላሽ ይፈልጋሉ፡፡ እንደ ከዚህ ቀደሙ ተወስነው የማይተገበሩ ውሳኔዎች፣ ሊራመዱ የማይችሉ አቋሞች ሊሆኑ አይገባም፡፡ ለተግባራዊነቱ ደግሞ ከብፁዓን አባቶች ጀምሮ በርካታ የቤተ ክህነቱ አካላት ድጋፍ እንዳላቸው ቅዱስነታቸው አቋማቸውን በንግግራቸው ባንጸባረቁበት ወቅት በሰጡት ሞቅ ያለ የድጋፍ ምላሽ መረዳት ይቻላል፡፡ ከጥቂት ራስ ወዳዶች በስተቀር የቤተ ክርስቲያኒቱ አገልግሎት ማሻሻያን በብርቱ የማይፈልግ የለም፡፡ በአስቸኳይና በጥብቅ ይፈልገዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱ ገጽታ እንዲጎድፍ የሚሻ የለም፡፡ የጎደፈም ነገር ካለ በፍጥነት ማስተካከያ ለማድረግ መረባረብ ይገባል፡፡ የእርምጃው ቁልፍ ያለው ግን በቅዱስ ሲኖዶስ ጥብቅ አቋም ላይና በቅዱስ ፓትርያርኩ የአስተውሎት ርምጃ ውስጥ ነው፡፡

ለውጥን ምእመናንን በመላው፣ ማኅበረ ካህናቱ በየደረጃው፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶችና ማኅበራት፣ አድባራትና ገዳማቱ፣ ተማሪዎችና መምህራኑ፣ ደቀመዛሙርቱና መዘምራኑ ሁሉ በብርቱ ይፈልጋሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያን የዕረፍት ወደብ መሆን አለባት፡፡ እንደ ቅዱስነታቸው ንግግርም ለቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን ለሀገርም አርአያ መሆን፣ ለዓለሙ ጨው መሆን አለባት፡፡ አሮጌው ነገር ሁሉ ማለፍ አለበት፤ አዲሱ መልካሙ ነገር ሁሉ ሊመጣ ይገባል፡፡ በዚያን ጊዜ ሁሉም አንድ ሆኖ ያስባል፡፡ መንፈሳዊው ሥራ ይሠለጥናል፤ የሥጋው ሥራ ወደ ቤቱ ይመለሳል፡፡

ዛሬ በየአህጉራቱ ያሉ የኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት በብርቱ ተነቃቅተው የዓለምን ብልሹ ነገር ሁሉ እየተዋጉ ነው፡፡ ጠንካራ አደረጃጀትና የአግልግሎት አድማስ ፈጥረው እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ፡፡ የታሪክ፣ የሞራል፣ የዕውቀት፣ የሥነ ምግባርም መሠረት ያላት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ይሔንን አቅም ፈጥሮ ለመንቀሳቀስ የሚያግዳት አንዳችም ነገር የለባትም፡፡ ዋናውና ወሳኙ ነገር የእግዚአብሔርን ቡራኬ ማስገኘት የሚችል በጎ ምግባር፣ ቀና ሐሳብ ቤተ ክህነቱ ይዞ የመገኘቱ ነገር ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ጥቂቱ ብዙ፣ ጥቁሩ ነጭ፣ ክፉው ሁሉ ለመልካም የማይሆንበት ምክንያት እንደማይኖር ማኅበረ ቅዱሳን የጸና አቋም አለው፡፡

በአጠቃላይ ቅዱስነታቸው ያመላከቱንን በጎ መንገድ መከተል ቤተክርስቲያን ያለ አማራጭ ይዛው ልትገኝ የሚገባት አካሄድ ነው፡፡ ለዚህ ጥሪ ምላሽ መስጠት ደግሞ የሁሉም የቤተ ክርስቲያን ቤተሰብ ሓላፊነት ነው፡፡ የማኅበረ ቅዱሳን አባላትም ለዚሁ ጥሪ በጎ ምላሽ ለመስጠት መዘጋጀታቸውን በዚሁ አጋጣሚ ለመግለጽ እንወዳለን፡፡

 

ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት 21ኛ ዓመት ቁጥር 1 ግንቦት 2005 ዓ.ም.

ወስብሐት ለእግዚአብሔር           

te 30

በባሕረ ጥበባት /Encyclopedia of EOTC/ ዝግጅት ዙሪያ የምክክር ጉባኤ ተካሔደ

ግንቦት 30 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል አስተባባሪነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የባሕረ ጥበባት /Encyclopedia of EOTC/ ዝግጅት ዙሪያ ከባለ ድርሻ አካላት ጋር የምክክር ጉባኤ ተካሔደ፡፡

ግንቦት 29 ቀን 2005 ዓ.ም. ከቀኑ አስር ሰዓት ጀምሮ በሰሜን ሆቴል በተካሔደው የምክክር ጉባኤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ባሕረ ጥበባት /Encyclopedia of EOTC/ ማዘጋጀትte 30 ያስፈለገበት ዋነኛ ምክንያትን አስመልክቶ በማኅበሩ ሰብሳቢ በቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ ተገልጿል፡፡ በንግግራቸውም በተለያዩ ጊዜያት የቤተ ክርስቲያኒቱን ታሪክና ቅርሶች አጥኚዎች፤ ጎብኚዎችና ምእመናን መረጃዎችን ማእከላዊና ሕጋዊ ከሆነ ቦታ ማግኘት አስቸጋሪ መሆኑን አውስተው አለም አቀፍ ተቀባይነት ያለው፤ ሊቃውንቱ የሚያውቁት የቤተ ክርስቲያንን ማንንት የሚገልጽ መረጃ ማዘጋጀት፤ በተለያዩ ጊዜያት በዘርፉ የተሞከረው እውቀት በአንድ ላይ በማሰባሰብ የታሪክ ቅሰጣ ለማስቀረትና ለመከላከል እንዲቻል ይህንን ባሕረ ጥበባት ማዘጋጀት እንዳስፈለገ አብራርተዋል፡፡  

በተካሔደው ውይይትም የሚዘጋጀው ባሕረ ጥበባት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት፤ ታሪክና ሥርዓት እንዲይዝ እንዴት ተደርጎ ይዘጋጃል፤ ማነው የሚያዘጋጀው፤ አቅም / የሰው ሃይል፤ten 30 ገንዘብ . . ./ ፤ ተጀምሮ እንዳይቋረጥ ምን መደረግ አለበት፤ የባለሙያዎች ድጋፍ፤ የባለ ድርሻ አካላት ትብብር፤ የአሰራር ሥልቶች ዝግጅት፤ በስንት ጊዜ ይጠናቀቃል? በሚሉና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ሰፋ ያለ ውይይት ተካሒዷል፡፡

በመጨረሻም በአማርኛና በእንግሊዝኛ የሚዘጋጀው የዚህ ባሕረ ጥበባት ባለቤት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስትሆን ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ባለድርሻ አካላትን በማስተባበር በገንዘብ በጊዜ በሰው ኃይል የተቀናጀ አደረጃጀት ያለው ሆኖ ሥራውን ግን ማኅበረ ቅዱሳን  በበላይነት ቢመራው የተሻለ እንደሚሆን አስተያየት ቀርቧል፡፡ ለሥራው ግብአት የሚሆኑ አሳቦችንም ለማሰሳሰብ የምክክር ጉባኤው በተደጋጋሚ እንደሚደረግ ተጠቅሷል፡፡

tena
በምክክር ጉባኤው ላይ ከሊቃውንት ጉባኤ፣ ከአዲስ አበባ ዮኒቨርሲቲ፣ ከቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳዊ ኮሌጆች፤ ከቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን፤ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ቤተ መዛግብትና መጻሕፍት ኤጀንሲ፣ ከአዲስ አበባ ባሕልና ቱሪዝም ቢሮ፣ እንዲሁም የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራርና ሥራ አሰፈጻሚ አባላት ተገኝተዋል፡፡

senod 2005

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ተጠናቀቀ

ግንቦት 30 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

senod 2005

ከግንቦት 21 ቀን ጀምሮ እስከ ግንቦት 30 2005 ዓ.ም.  ድረስ ሲካሔድ የሰነበተው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ለቤተ ክርስቲያኗ አስፈላጊ ናቸው ያላቸውን ውሳኔዎች በማሳለፍ ተጠናቀቀ፡፡ በዚህም መሠረት የሚከተሉትን ጠቅለል ያሉ ውሣኔዎች ተላልፈዋል፡፡  በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ የሚታዩ ብልሹ የአስተዳደርና የአሰራር ችግሮችን  ማሻሻል፤ ጥራት የጎደለው የፋይናንስ አያያዝን መዋጋት፤ ሙስናንና ለብክነት የተጋለጡ አሰራሮችን ለመቅረፍ እንዲቻል ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ ምሁራንና ምእመናን የሚገኙበት ዓብይ ኮሚቴ ማዋቀሩን ይፋ ማድረግ፡፡ በተጨማሪም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በአንድ ሀገረ ስብከት፤ በአንድ የቅዱስ ፓትርያርክ ረዳት ሊቀ ጳጳስ እንዲመራ የተደረገ ሲሆን ፤ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊ ምርጫም ተከናውኗል፡፡ ከሀገር ውጪ ከሚገኙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ጋር የተጀመረው የሰላም ውይይት ጥረት እንደሚቀጥልም የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

ዝርዝር መግለጫውን ከዚህ በታች እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡

 

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

    በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 164 ላይ ከበዐለ ትንሣኤ በኋላ በሃያ አምስተኛው ቀን  ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እንዲካሔድ በተደነገገው ቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ከግንቦት 21 – 30 ቀን 2005 ዓ.ም. ተካሒዷል፡፡ ይህ ጉባኤ የርክበ ካህናት ጉባኤ ተብሎ የሚታወቅ ሲሆን ከላ በተጠቀሰው ቀኖና ቤተ ክርስቲያን እንደተገለጸው ብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት በቤተ ክርስቲያን ያለውን አጠቃላይ መንፈሳዊ፤ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ጉዳዮችን በማየት በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ታላላቅ ውሳኔዎችን የሚወሰንበት ዓብይ ጉባኤ ነው፡፡

    ቅዱስ ሲኖዶስ በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ያሉትን ወቅታዊና ነባራዊ ጉዳዮችን ለመመርመርና ለመገምገም ባለው ሐዋርያዊ ኃላፊነት ለቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ ተልእኮ አፈጻጸም እንቅፋት ናቸው ብሎ ያመነባቸውን ጉዳዮች በአጀንዳ ቀርጾ፤ በስፋትና በጥልቀት ተወያይቶ ውሳኔ ሰጥቶባቸዋል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በምድር ላይ ያለች የእግዚአብሔር መንግስት ማዕከል፤ በባሕርይዋም ንጽሕትና ቅድስት ብትሆንም ኃጢአትና ስሕተት በነገሰበት ዓለም ያለች በመሆንዋ ከእርስዋ መሠረታዊ ባሕርይ ጋር የማይስማሙ ተግባራት እንዳይጋቡባት የመጀመሪያው ጥበቃ በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ላይ ያረፈ ነው፡፡ በተለይም የአሁኑ ዓላማችን ጥበብ ባፈራው የአሠራር ዕውቀት በየቀኑ በለውጥ ጎዳና በሚራመድበት ጊዜ ቤተ ክርስቲያናችንም ከዓለሙ በተሻለና በበለጠ በመንፈሳዊና በአእምሮአዊ ጥበብ ሕዝበ ክርስቲያኑን መምራት፤ ማስተማርና ማገልገል ይጠበቅባታል፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን እነዚህን የተቀደሱ ተግባራት በሥራ ለመተርጎም ወቅታዊ እንቅፋት ሊሆኑ የሚችሉ ነገሮች ምን ምን ናቸው? በማለት ቅዱስ ሲኖዶስ በጥልቀት ተመልክቶአል፡፡

    በዚህ መሠረት ጉባኤው ብዙ ውይይት ካደረገ በኋላ የሚከተሉትን ዓበይት ውሳኔዎችን አሳልፎአል፡፡

 

  1. በየሥራ ዘርፉ እየተከሠተ ያለው የመልካም አስተዳደርን ችግር በተለይም ብልሹ አስተዳደርና አሠራር፤ ዘመኑን ያልዋጀና ጥራት የጎደለው የፋይናንስ አያያዝ፤ እንደዚሁም ለሙስናና ለብክነት የተጋለጡ አሠራሮች ሁሉ ወሳኝ በሆነ መልኩ ለመቅረፍና ለማድረቅ፣ ከዚህም ጋር ቤተ ክርስቲያናችን በመሪ እቅድ መሥራት የምትችልበትን አሠራር ለመቀየስ፣ ቅዱስ ሲኖዶስ፡- ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ምሁራን ምእመናን የሚገኙበት ዓቢይ ኮሚቴ ተቋቁሞ ጉዳዮን የማጣራትና የማጥናት ሥራውን እንዲቀጥል ተስማምቶ በአንድ ድምፅ ወሰኖአል፡፡

  2. የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ለሌሎች አህጉረ ስብከት በመልካም አስተዳደርና በፋይናንስ አያያዝ፣ እንደዚሁም በስብከተ ወንጌልና በአገልግሎት አሰጣጥ ለሌሎች እንደዚሁም በመልካም አስተዳደር፣ በፋይናንስ አያያዝና በሰው ኀይል አመዳደብ የሕግ የበላይነትን አክብሮ እንዲሠራ አስፈላጊውን ክትትል ሁሉ በቋሚ ሲኖዶስና በመንበረ ፓትርያርኩ ጥብቅ ክትትል እንዲደረግ፤

  3. የቤተ ክርስቲያናችን የሕይወት ምንጭ የሆነውን የስብከተ ወንግል ትምህርት በሰው ኀይል፣ በሚድያም ጭምር እየታገዘ በመላው ዓለም ላሉ የቤተ ክርስቲያናችን ተከታዮች ትምህርቱን በጥራትና በጥልቀት ይሰጥ ዘንድ አስፈፋሚው አካል ጠንከር ያለ ሥራ እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ምርጫ በየሦስት ዓመቱ እንዲካሄድ ሕገ ቤተ ክርስቲያን ባስቀመጠው ድንጋጌ መሠረት ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፤ የወላይታ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፤ የሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ አድርጎ ቅዱስ ሲኖዶስ መርጧቸዋል፡፡

  4. ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የጅማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ሆነው እንዲሠሩ፤ እንደዚሁም የምራቅና ሰሜን አዲስ አበባ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዳንኤል በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዳንኤል በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ሆነው እንዲሠሩ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

  5. በመካከለኛው ምሥራቅና በሌሎች የዓለም ክፍሎች ለሥራ ፍለጋ በሕገ ወጥ መንገድ በሚሄዱ ልጆቻችንና ወገኖቻችን ላይ እየደረሰ ያለውን ዘግናኝ ድርጊት ለማስቆም መንግሥት እያደረገ ያለው ጥረት ቤተ ክርስቲያናችን በሙሉ ልብ እንደምትደግፈውና ለስኬቱም የበኩሏን እንደምትወጣ፣ ለዚህም በየደረጃው ያሉ መምህራን፣ ካህናትና ሰባክያን ሁሉ የዚህን ጎጂነት ደጋግመው በማስረዳትና በማስተማር ሕዝቡ ግንዛቤ እንዲኖረው ጠንክረው እንዲያስተምሩ ቅዱስ ሲኖዶስ መመሪያ ሰጥቷል፡፡

  6. የሀገራችን ሕዝቦች ከድህነትና ከኋላ ቀርነት ተላቀው መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገሮች ጋር እኩል ለማሰለፍ በሚደረገው ሁለንተናዊ የልማት ተግባር ቤተ ክርስቲያናችን ከሕዝቡና ከመንግሥት ጎን በመሆን የሚጠበቅባትን ሁሉ እንደምታደርግ ቅዱስ ሲኖዶስ አረጋግጧል፡፡

  7. ኢትዮጵያ ሀገራችን በሀገር ውስጥ፣ በምሥራቅ አፍሪካ፣ በመላ አፍሪካ ከዚያም በመላው ዓለም ሰላም እንዲሰፍን፣ የሰው ልጅ እኩልነትና መብት እንዲከበር፣ ፍትሐዊ የሆነ የሀብት አጠቃቀም እንዲኖር፣ የአየር መዛባትን ለመቋቋም የአረንጓዴ ልማት ሀብት እንዲስፋፋ የምታደርገውን ያላሰለሰ ጥረት ቅዱስ ሲኖዶስ በእጅጉ እያደነቀ የሀገሪቱን መልካም ዝናና በጎ ገጽታ ለመጠበቅ የበኩሉን ጠንክሮ እንዲሠራ አረጋግጧል፡፡

  8. በሀገራችን የዕድገት ሂደት ከፍተኛ ሚና ይጫወታል ተብሎ በመገንባት የሚገኘው ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ሥራው ተጠናቆ ጥቅም ላይ እስኪውል ድረስ ቤተ ክርስቲያናችን አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ እንደማታቋርጥ ቅዲስ ሲኖዶስ ያረጋግጣል፡፡

  9. ሀገራችን ኢትዮጵያ በጤናው ዘርፍ የኅብረተ ሰቡን ጤንነት ለመጠበቅ በተለይም በሀገር አቀፍ ደረጃ ለእናቶችና ለሕፅናት እየተደረገ ያለው ልዩ የጤና እንክብካቤ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ቤተ ክርስቲያናችን ኅብረተሰቡን ከማስተማርና የጉዳዩን ጠቃሚነት ከማስረዳት ባሻገር ለመርሐ ግብሩ መሳካት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደምታደረግ ቅዲስ ሲኖዶስ ይገልፃል፡፡

  10. ከሀገር ውጭ ከሚገኙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ጋር የተጀመረው የላም ውይይት በተለያዩ ምክንያቶች እስካሁን የሚፈለገውን የአንድነት ውጤት ባያስገኝም የቤተ ክርስቲያናችን አንድነትና ሰላም ለቤተ ክርስቲያናችንም ሆነ ለሀገራችን እንዲሁም ለሕዝባችን ያለው ትርጉም የላቀ መሆኑን ቅዲስ ሲኖዶስ ስለሚገነዘብ ሁኔታዎች ተመቻችተው የሰላም ውይይቱ እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

  11. ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቲያኒቱን መንፈሳዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ተልእኮ ዘመኑ በሚጠይቀው ጥበብና ዕውቀት እየቃኘ ለሃይማኖት፣ ለሀገርና ለሕዝበ ክርስቲያኑ ማበርከት የሚገባውን ሁሉ በብቃት ለመሥራት ከምንም ጊዜ በላይ የተዘጋጀ መሆኑን ሕዝበ ክርስቲያኑቀ ተገንዝቦ እርሱም የበኩሉን ሥራ በቅን መንፈስ እንዲወጣ አበክሮ አሳስቧል፡፡

የቤተ ክርስቲያናችን የመጨረሻ ውሳኔ ሰጭ የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ በየጊዜው የሚያስተላልፋቸው ውሳኔዎችና መመሪያዎች ሁሉ ተፈጻሚነት ኖሮአቸው ጥሩ ውጤት ሊያስገኙ የሚችሉት በሁሉም ደረጃና አካባቢ የሚገኙ የቤተ ክርስቲያናችን ካህናትና ምእመናን ለቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ተግባራዊነት በሙሉ ልባዠው ሲሰለፉ እንደሆነ የቅዱስ ሲኖዶስ እምነት ነው፡፡ ስለሆነም ለእናት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ክብርና ሉዓላዊነት መጠበቅ፣ ለሕልውናዋ መቀጠልና ለዕድገትዋ መስፋፋት የሚቆረቆሩ የቤተ ክርስቲያናችን አገልጋዮችና ተከታዮች በሙሉ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚያሳልፋቸውን ውሳኔዎችና መመሪያዎች ለመተግበር አስፈላጊውን ትብብር ሁሉ እንዲያደርጉ በአጽንዖት በማሳሰብ ለዐሥር ቀናት ያህል ሲካሄድ የሰነበተውን ጉባኤ ዛሬ ግንቦት 30 ቀን 2005 ዓ.ም. በጸሎት አጠናቅቋል፡፡

እግዚአብሔር ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንንና ሀገራችን ኢትዮጵያን ይባርክ፤ ይቀድስ፤ አሜን!!

 

አባ ማትየስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
ግንቦት 30 ቀን 2005 ዓ.ም.

hamela 5

የጀበራ ማርያም ገዳምን እንደገና ለማቋቋም ጥረት በመደረግ ላይ ነው

ግንቦት 3ዐ ቀን 2ዐዐ5 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በበሰሜን ጎንደር ዞን ደንቢያ ወረዳ በጣና ሐይቅ ደሴቶች ውስጥ ከሚገኙት ገዳማት አንዱ የሆነውና ለረጅም ዘመናት ጠፍ ሆኖ፤ ፈርሶ የቆየው የጀበራ ማርያም ገዳምን መልሶ ለማቋቋም ጥረት በመደረግ ላይ ነው፡፡

hamela 5የጀበራ ማርያም ገዳም በአፄ አምደ ጽዮን ዘመነ መንግሥት በ13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተገደመ ሲሆን በደርቡሽ ወረራ ወቅት ከፍተኛ ጉዳት ደርሶበት ሙሉ ለሙሉ ፈርሷል፡፡ ነገር ግን አባቶች መልሰው ገዳሙን በመመሥረት አጽንተውት የነበረ ቢሆንም የኢጣሊያ ጦር ኢትዮጵያን ሲወርር በ1956 ዓ.ም. መምህር ካሳ ፈንታ በሚባሉ አባት ቤተ ክርስቲያኑን በማነጽ፤ ገዳሙን መልሶ በመገደም ጥንት ወደነበረበት ለመመለስ ጥረት አድርገው ነበር፡፡ ነገር ግን እሳቸው ካረፉ በኋላ ከእግራቸው ተተክቶ ገዳሙን አጠናክሮ ለመያዝ የሚችል  አባት በመጥፋቱ ገዳሙ ተፈታ፡፡ የቤተ ክርስቲያኑም እንጨት በምስጥ ተበልቶ በንፋስ ኃይል ስለፈረሰ ታቦቱ ከሐይቁ ማዶ በምትገኘው ቅድስት ሃና ማርያም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዲገባ ተደርጓል፡፡

ገዳሙን መልሶ በማቅናት ላይ የሚገኙት አባ ዘወንጌል በገዳሙ ውስጥ ከዚህ ቀደም ለሦስት ዓመታት ቆይተው፤ በችግር ምክንያት በመውጣት ወደ ዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ከሔዱ 20 ዓመት ሆኗቸዋል፡፡ “የገዳሙ መፈታት በመስማቴና ህሊናዬ ሊያርፍ ባለመቻሉ አባቶቻችን ያቆዩልንን ገዳም ዳግም ለመመሥረት ወደዚህ መጣሁ፡፡ ከመጣሁም ገና 3 ወራት ብቻ ናቸው የተቆጠሩት” ይላሉ፡፡

በሦስት ወራት ውስጥ ቤተልሔምና ቤተ እግዚአብሔር /ምግብ ማብሰያ/ ተሰርተው ተጠናቀዋል፡፡ በቀጣይነትም ለመናንያን በዓት፤ የእንግዳ ማረፊያ ቤት፤ ከደሴቱ ማዶ በሚገኘውና የገዳሙ ይዞታ በሆነው አንደhamela 4 ሄክታር መሬት ላይ የሞፈር ቤት ለመሥራት በእንቅስቃሴ ላይ ይገኛሉ፡፡ እነዚህ ሥራዎች እንደተጠናቀቁም በጅምር ላይ የሚገኘውን ቤተ ክርስቲያን ለማነጽ ጥረት እንደሚያደርጉ አባ ዘወንጌል ይገልጻሉ፡፡

ጀበራ ማርያም ገዳም ውስጥ በጾም በጸሎት ተወስነው የሚገኙ አባቶች በጸሎታቸው ወቅት  እጆቻቸው እንደ ከዋክብት ያበሩ ስለነበር በአካባቢው የሚገኙ ምእመናን “እጀበራዎች” እያሉ ይጠሯቸው  ስለነበር የገዳሙ ስያሜ ሆኗል፡፡ በአሁኑ ወቅት በገዳሙ ውስጥ ስድስት መናንያን ብቻ ,ይገኛሉ፡፡

hamela 3

የቅዱስ ሚካኤል ታቦት “ካህኑን” አቃጠለ

ግንቦት 30 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ

 

  • የአብያተ ክርስቲያናት ዝርፊያ ተባብሷል

hamela 3የሐምሌ ቅዱስ ሚካኤል ታቦት ግንቦት 2 ቀን 2005 ዓ.ም. ሌሊት በሌቦች ተዘርፎ ሲወሰድ መንገድ ላይ የዘራፊውን “ካህን” አእምሮውን አስቶ፤ መንገዱን አስትቶ፤ በሰው ማሳ ውስጥ እንዳስገባውና ታቦቱም ወደ ሰማይ እየዘለለ ዘራፊውን እንዳቃጠለ የሀባቦ ጉዱሩ ወረዳ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ትጉኀን ብዙዓለም ግንባር ተናገሩ፡፡

“እንዲሁም ተጠርጣሪው ‘ወየው ለእኔ፤ ወየው ለእኔ’ እያለ ሲጮህ በአካባቢው አትክልት ሲጠብቁ ያደሩ ሰዎች እንደሰሙ እና ተጠርጣሪው እስር ቤት ከገባ በኋላም ‘እባቦች እየመጡብኝ ነው’ እያለ ለፖሊስ እንደሚያመለክት፤ ፖሊሶችም ወደ ታሰረበት ክፍል ሲገቡ ምንም እባብ እንዳላገኙ” ሊቀ ትጉኀን ብዙዓለም የቅዱስ ሚካኤልን ድንቅ ተአምር መስክረዋል፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ ታቦት ድንቅ የሆነ ገቢረ ተአምራትን እንደሚያደርግ የተጠቀሰ ነው፤ ያሉት ደግሞ በጉዱሩና በሀባቦ ጉዱሩ ወረዳዎች በሰባኬ ወንጌልነት የሚያገለግሉት ቆሞስ አባ ወልደ ገብርኤል አበበ ሲሆኑ፤ የሐምሌ ቅዱስ ሚካኤል ታቦትም ገቢረ ተአምሩን ሊሰርቅ በሞከረው “ካህን” ላይ አሳይቷል ብለዋል፡፡

የሐምሌ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ቄስ ዋለ ዓለሙ ስለ ሐምሌ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን የዘረፋ ሙከራ እንዳመለከቱት “በዕድሜ ዘመኔ እንዲህ ያለ ነገር ተመልክቼ አላውቅም፡፡ በዚህ ዓመት ብቻ የሐምሌ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ሁለት ጊዜ (ኅዳር 10 እና ግንቦት 2 ቀን 2005 ዓ.ም) ተዘርፏል፡፡ የግንቦት ሁለት ቀን ግን ለየት ያለ ነበር፡፡ በዕለቱ ታቦት፣ ሙዳየ ምጽዋት፣ መስቀልና መጽሐፍ ባልታወቁ “ካህናት” ተዘርፈው ታቦቱ ከአንድ ኪሎ ሜትር ርቀት በላይ ተወሰዶ በአንድ ሕፃን ልጅና በሦስት ሴቶች ተገኝቷል”  በማለት አስረድተዋል፡፡

የተዘረፈውን ታቦት የእርሻ ማሳ ውስጥ ተቀምጦ ከተመለከቱት ልጆች መካከል ብዙነሽ ዓለማየሁ ስለሁኔታው ስትናገር “አራት ሆነን በአህያዎቻችን ዕቃ ጭነን ወደ ገበያ ስንሄድ ከሐምሌ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን አካባቢ ካሉ የእርሻ ማሳ ደረስን፡፡ በዚህን ጊዜ አብሮን የነበረው ሕፃን የቤተ ክርስቲያን መጽሐፍ የሚመስል ነገር አየና ለእኛም አሳየን፡፡ እኛም ወንጌል መስሎን ለመሳለም አንሥተን ለመሳለም ስንሞከር አቃተን፤ አንቀጠቀጠን፡፡ ፈርተን አህዮችን ነድተን ልንሄድ ስንል አህዮች ቀድመው ስለወደቁ መነሣት አልቻሉም፡፡ አህዩችን ለማስነሣት ብንሞክርም አልተቻለም፡፡ በመጨረሻ ነገሩ ተአምር መሆኑን ስለተረዳን ለዲያቆናት ስልክ ደወልን” በማለት ምስክርነቷን ሰጥታለች፡፡

ወንጌል መስሏት ለመሣለም የፈለገችው እንሰኔ ዓለማየሁ ስለተመለከተችው ተአምር ስትገልጽ “ጠጋ ብዬ ላነሣው ስሞክር ቀኝ እጄን አሸማቀቀኝ፣ ለዲያቆን ታደለ ደወልን፤ እርሱ መጥቶ ታቦቱ ላይ ፎጣውን አልብሶ ካህናት ሊጠራ ሔደ፤ ከፎጣው ብርሃን ሲወጣ ስንመለከት፤ ታቦቱ የተቃጠለ መሰሎን አለቀስን፤ ታቦቱ ግን ምንም አልሆነም” ብላለች፡፡ አያይዛም ታቦቱን አስቀድሞ የተመለከተው ሕፃን ሌሊቱን ሙሉ ሲባንን ማደሩን አውስታለች፡፡

የሬፍ ቶኮ ታኔ ቀበሌ ገበሬ ማኅበር ሊቀ መንበር ኮንስታብል ደረጀ ጉቱ ስለሁኔታው  ሲያስረዱ “የቤተ ክርስቲያኑን መሰበር የሰማነው ከጠዋቱ ሁለት ሰዓት ላይ ሲሆን፤ ታቦቱንም ሚግሮ ዳሞት አካባቢ ወድቆ፤ በአካባቢውም መዝሙረ ዳዊትና የተሰበሩ ሦስት ባንኮኒዎችን አገኘን፡፡ በመዝሙረ ዳዊቱ ላይ ባገኘነው ማስታወሻ መሠረት ተጠርጣሪውን ልንይዝ ችለናል” ብለዋል፡፡

“ታቦቱን ካለበት ቦታ ማን ያነሰዋል እያልን ስንመካከር ከመካከላችን የነበረ አንድ የሌላ እምነት ተከታይ ‘እኔ አነሣለሁ’ ብሎ ቀረበ፤ ነገር ግን ታቦቱን ሲቀርብ ፈራ፤ ‘ሰውነቴን አቃጠለኝ ራሴን አቃጠለኝ እንደ አንድ ነገር አደረገኝ’ ብሎ በመደንግጥ ሄደ” በማለት ኮንስታብል ደረጀ ተናግሯል፡፡

hamela 2
ታቦታቱን ለማክበር ከመጡት አባቶች መካከል ቆሞስ አባ ወልደ ገብርኤል ስለሁኔታው ሲናገሩ “ታቦቱን ዘራፊው አስቀምጦት የሄደበት ቦታ ዙሪያ ገባው ጭቃ ነበር፡፡ ይህ ጭቃ ታቦቱን ሳይነካ በታቦቱ ዙሪያ መሆኑ የሚያመለክተው ታቦቱ ሌባውን አስሮት ማቆየቱና ሌባው ታቦቱን በዙሪያው ሲዞር ማደሩን የሚያመለክት ነው” ሲሉ አስገንዝበዋል፡፡

ታቦቱ የተገኘው በእኛ የእርሻ ማሳ ላይ ነው፤ የሚሉት የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ የሆኑት ግለሰቦች በበኩላቸው “ታቦቱ እኛ ማሳ ጋር ሲደርስ አልሄድም ማለቱ እግዚአብሔር ስለወደደን ነው፡፡ ይህ ታቦቱ ያረፈበት መሬት የበረከት መሬት ነው” ሲሉ ታቦቱ የተገኘበትን ቦታ ከልለው ለቤተ ክርስቲያን መስጠታቸውን ተናግረዋል፡፡

ታቦተ ሚካኤል ድንቅ የሆነ ሥራውን በዐደባባይ ሠርቶ በሆታና በዝማሬ ግንቦት 3 ቀን 2005 ዓ.ም ወደ መንበረ ክብሩ መመለሱን ቄስ ጋሸነው እንዳላማው አስታውቀዋል፡፡

በተያያዘም ሊቀ ትጉኀን ቀሲስ ብዙዓለም በወረዳቸው ስለተፈጸሙ የአብያተ ክርስቲያናት ዘረፋ እንዳስታወቁት “ከሰኔ 2004 ዓ.ም እስከ ግንቦት 2005 ዓ.ም በወረዳው ካሉ ዐሥራ አንድ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ በፎቃ መድኀኔዓለም ቤተ ክርስቲያን፣ በእንባቦ ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን፣ ሎያ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን እና በሐምሌ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ላይ ሁለት ጊዜና ከዚያ በላይ ዘረፋና የዘረፋ ሙከራ ተካሂዶባቸዋል፡፡ እንዲሁም ብራና መጽሐፍት፤ መስቀሎች፤ መጋረጃዎችና መጎናጸፍያ እንዲሁም ሙዳየ ምጽዋቶች መወሰዳቸውን ተናግረዋል፡፡

የፎቃ መድኀኔዓለም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ የሆኑት ቄስ ዘላለም ጌትነት በበኩላቸው በፎቃ መድኀኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ላይ ከፍተኛ የሆነ የዘረፋ ሙከራ እየተደረገ በመሆኑ ለአገልግሎት መቸገራቸውን ተናግረዋል፡፡

የፎቃ መድኀኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ዘበኛ አቶ አሰፋ ትእዛዙ ከዘራፊዎቹ ስለገጠማቸው ጥቃት ሲናገሩ “ዓምና በግንቦት ወር ላይ ከምሽቱ አምስት ሰዓት አካባቢ ሦስት ሌቦች መጥተው የቤተ ክርስቲያኑን በር ነኩ፡፡ በራፉ ላይ ያስቀመጥኩት ቆርቆሮ መሳይ ነገር ወደ መሬት በመውደቅ ድምፅ አሰማኝ፡፡ እኔም በፍጥነት በመነሣት ባትሪ ሳበራ ሌቦቹ ጨለማውን ተገን አድርገው ወደ እኔ መጡ፡፡ በገጀራ ሊመቱኝም ሞከሩ፤ ነገር ግን በእግዚአብሔር ጥበቃ በትራቸውን ዛፉ ከለከለው፡፡ በመጨረሻም እግሬን በአንካሴ ወጉኝ፡፡” ብለው ዘራፊዎቹ የተደራጁ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

በተመሳሳይም በወረዳው ካሉ አብያተ ክርስቲያናት የዘረፋ ጥቃት ከደረሰባቸው አብያተ ክርስቲያናት መካከል አንዱ የእንባቦ ተክለሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን አንዱ ነው ያሉት ደግሞ አቶ ዘላለም ኩምሳ ናቸው፡፡

አቶ ዘላለም የእንባቦ ተክለሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን በንጉሥ ተክለ ሃይማኖት የታነጸና ረዥም ዕድሜ ያለው በመሆኑ ዘራፊዎችም ከፍተኛ ትኩረት ያደርጉበታል፡፡ ለዚህም ለሦስት ጊዜያት ያህል ሌቦች የዘረፋ ሙከራ እንዳካሄዱበትና የቤተ ክርስቲያኑን ቁልፍና ካዝና በመስበር መጋረጃዎች እንደተወሰዱ ተናግረዋል፡፡

በጥርጣሬ የተያዙ አካላትና መዝረፋቸውን ያመኑ ሰዎች አሉ የሚሉት ደግሞ የወረዳው የፖሊስ ናቸው፡፡ ቢሮው ማንኛውንም ችግሮች ለማስወገድ ቀን ከሌሊት እንደሚሠራና በየቀበሌው ፖሊስ በማስቀመጥ፣ ለሕዝቡ ስለ ሌብነት በማስተማር፣ ለጥበቃ አካላት ሥልጠና በመሥጠት እንደ ሀገር ይሠራል፡፡” ብለዋል፡፡

አያይዘውም “በጥርጣሬ የተያዙ ሌቦችንም ማስረጃ አቅርበን ተገቢውን ፍርድ እንደሚያገኙ እናምናለን  ሕዝቡም ሊተባበር ይገባል” ሲሉ አሳስበዋል፡፡

የሀባቦ ጉዱሩ ወረዳ ቤተ ክህነት የሚገኘው ከአዲስ አበባ በስተ ምዕራብ በቀድሞው ወለጋ ሀገረ ስብከት በአሁኑ ደግሞ ሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ሀገረ ስብከት ተብሎ በሚጠራው ሥር ሲሆን በወረዳ ቤተ ክህነቱ ሥር አሥራ አንድ አብያተ ክርስቲያናት መኖራቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ 

libraries

የመጻሕፍት ማሰባሰቢያ ሳምንት ተዘጋጀ

ግንቦት 23 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

libraries“አንድ መጽሐፍ ትውልድን ለመቅረጽ” በሚል መሪ ቃል በማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል አስተባባሪነት የማኅበሩን ቤተ መጻሕት በዘመናዊ ሁኔታ ማደራጀትና ክምችቱን ለማሳደግ፤ እንዲሁም ታላቅ የመረጃ ማእከል ለማድረግ ከሰኔ 1 እስከ 22 ቀን 2005 ዓ.ም. የሚቆይ የመጻሕፍት፤ የኮምፒዩተርና የመዛግብት ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር እንደተዘጋጀ የጥናትና ምርምር ማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር አቶ ሰይፈ አበበ ገለጹ፡፡

ቤተ መጻሕፍቱ ከማኅበሩ አባላትና ምእመናን በተለገሱ ጥቂት መጻሕፍት በ1998 ዓ.ም. በአነስተኛ መጠለያ /ኮንቴነር/ ውስጥ አገልግሎት መስጠት መጀመሩን፤ በወቅቱም የማኅበሩን አገልግሎትና ጥረት የተረዱት ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ የነበሯቸውን 400 መጻሕፍት በመለገስ እንዲጠናከር የበኩላቸውን ድርሻ መወጣታቸውንና በአሁኑ ወቅት 5000 የሚደርሱ የታተሙ ቅጂ /Hard copy/፤ 1100 ያልታተሙ ቅጂ /Soft copy/ እና 10 የሚደርሱ የተለያዩ የብራና መዛግብት የመረጃ ክምችት ቤተ መጻሕፍቱ እንዳለው አቶ ሰይፈ አበበ ገልጸዋል፡፡

ዓላማውን አሰመልከቶ ሲገልጹም “ማኅበሩ ቤተ መጻሕፍቱን በማጠናከር ዘመናዊ በማድረግ መጻሕፍት፤ ቤተ መዛግብትና ቋሚ ዐውደ ርዕይ /ሙዚየም/ ማቋቋም፤ በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ መልክ የሚገኙ የመረጃ ምንጮችን ማሰባሰብ፤ ማደራጀትና ለምእመናንና ለተመራማሪዎች አገልግሎት መስጠት ነው” ብለዋል፡፡ በተጨማሪም በልዩ በልዩ ቦታዎች /በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ሀገር/ የሚገኙ ከመሰል ቤተ መጻሕፍት ቤተ መዛግብት ጋር ግንኙነት በመፍጠር ጠቋሚ /ዳይሬክቶሪ/ ማዘጋጀት ከዓላማዎቹ መካከል አንዱ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

ቤተ መጻሕፍቱ ወደፊት በዘመናዊ መልኩ በማደራጀት የE- Library አገልግሎት መጀመር፤ የመረጃ ክምችቱን በ40 ሺሕ ማሳደግና በሶፍትዌር ማደራጀት፤ የዲጂታል ቤተ መጻሕፍት ማቋቋምና የዲጂታላይዜሽን ሥራ ለማከናወን ከፍተኛ እንቅስቃሴ እየተደረገ እንደሚገኝ  አክለው ገልጸዋል፡፡

ከአገር ውስጥ ማእከላት 10 ሺሕ፤ ከውጪ ማእከላት 10 ሺሕ፤ ከአባላትና ምእመናን 20 ሺህ የተለያዩ መጻሕፍት የሚጠበቅ ሲሆን መዛግብት በታተመ ቅጂ /Hard copy/፤ ባልታተመ ቅጂ /Soft copy/ በስጦታ መስጠት፤ ኮምፒዩተር፤ ስካነር፤ ፎቶ ኮፒ፤ ወዘተ . . . ቁሳቁሶችንና መጻሕፍትን ለመግዛት የሚያስችል ገንዘብ በመለገስ ተሳትፎ እንዲያደርጉ የጥናትና ምርምር ማእከል ምክትል ዳይሬክተሩ አቶ ሰይፈ አበበ አሳስበዋል፡፡