001a

ወቅታዊውን ጉዳይ አስመልክቶ ቅዱስ ሲኖዶስ መግለጫ አወጣ

ጥር 9 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኩኖአምላክ

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ወቅታዊውን ጉዳይ በማስመልከት፤ ትናንት ረቡዕ ጥር 8 ቀን 2005 ዓ.ም ባወጣው ባለ 5 ገጽ መግለጫ፥ በ3 ዐበይት ጉዳዮች ላይ ውይይት አድርጎ  ውሳኔ አሳልፏል፡፡

 

ቅዱስ ሲኖዶስ የመከረባቸውን አጀንዳዎችና ያተላለፈውን ውሳኔ የያዘው የመግለጫውን ሙሉ ቃል  አቅርበነዋል፡፡

001a002b003c004d005e

ketera 2 1

ከተራ ምንድን ነው?

ጥር 9 ቀን 2005 ዓ.ም.

መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

ketera 2 1

ጥያቄ

በየዓመቱ የጥምቀት በዓል በድመቀት ይከበራል፡፡ ከበዓሉ በፊት የከተራ በዓል የሚከበርበትን ታሪካዊና ሃይማኖታዊ ፋይዳውን ብታብራሩልን

ዮስቲና ከአዲስ አበባ

መልሱ

ከተራ ከበበ ካለው የግእዝ ግሥ የወጣ ነው፡፡ ፍችው ውኃ መከተር፣ መገደብ ማለት ነው፡፡  የጥምቀት ዋዜማ ታቦተ ሕጉ ከቤተ መቅደስ ወጥቶ ውኃ ባለበት አካባቢ ስለሚያድር የየአጥቢያው ሕዝብ እየተሰበሰበ በወንዝ ዳር ወይም በምንጭ አካባቢ ድንኳን ይተከላል፡፡ ድንኳንም ከሌለ ዳስ ሲጥል ይውላል፡፡ የምንጮች ውኃ ደካማ በመሆኑ እንዲጠራቀም ይከተራል ጉድጓድ እየተቆፈረ ውኃው እንዳይሄድ ይገደባል፡፡

ketera 2 2“ከተራ” በመባል የሚታወቀው – ዋዜማው” ሠርግው /1981፣8/ እንደገለጹት “ከተራ” የሚለው ቃል “ከተረ ከበበ ካለው የግዕዝ ግስ የወጣ ነው፡፡ ከተራ ፍቺውም ውኃ መከተር፣ ወይም መገደብ ማለት ነው፡፡” ብለው ሲፈቱ፣ ደስታ ተከለ ወልድ /1962፣ 694/ ደግሞ  የጥምቀት ዋዜማ፣ ጥር 10 የጠራ ወራጅ ውኃ የሚከተርበት ታቦትና ሰው ወደ ዠማ ወንዝ የሚወርዱበት ጊዜ” ነው በማለት ይፈቱታል፡፡ ኪዳነ ወልድ ክፍሌም /1948፣ 555/ ከተረ የሚለውን ቃል በቁሙ፣  “ዘጋ፣ አቆመ፣ አገደ፣ ከለከለ፡፡” ማለት ነው ብለው ይፈቱታል፡፡ በየዓመቱ ጥር 10 ቀን የምእመናኑ አብዛኛው ሥራ ውኃውን መከተርና መገደብ በመሆኑ ዕለቱ ከተራ የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ ውኃው የሚከተረው በማግሥቱ ጥር 11 ቀን የጥምቀት በዓል ስለሚከበር ለሕዝቡ መጠመቂያ እንዲሆን ነው፡፡

 

በየሰበካው ቦታ ተለይቶና ተከልሎ ታቦታቱ በዳስ ወይም በድንኳን የሚያድሩበት፣ የተለያዩ የውኃ አካላት ተጠርገው የሚከተሩበት ወይም ሰው ሠራሽ የግድብ ውኃ የሚበጅበት ስፍራ ‹‹ባሕረ ጥምቀት››፣ ‹‹የታቦት ማደርያ›› እየተባለ ይጠራል፡ ባሕር፡- የውኃ መሰብሰቢያ (ምእላደ ማይ፣ የውኃ መከማቻ (ምቋመ ማይ) ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ‹‹የውኃ አገር›› /መካነ ማይ፣ ዓለመ ማይ/ ነው፡፡

 

ከዚህም በተጨማሪ በቅዱስ ላልይበላ ዘመነ መንግሥት በኢትዮጵያ ምድር እየተመላለሱ በብሕትውና እና በስብከተ ወንጌል  ያገለግሉ የነበሩት ጻድቁ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በአክሱም፣ በመቐለና በመርጡለ ማርያም እየተዘዋወሩ ባሕረ ጥምቀቱን ባርከዋል፡፡ በዐፄ ይኩኖ አምላክ ዘመነ መንግሥት (1260-1275 ዓ.ም) በጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት (1203-1204 ዓ.ም) አሳሳቢነት የተጀመረው ሥርዐተ በዓል ተጠናክሮ እንዲቀጥል በዐዋጅ ትእዛዝ አስተላልፈዋል፡፡ ታቦታቱም በሕዝብ ጥበቃና ክብካቤ ተደርጎላቸው በየጥምቀተ ባሕሩ እንዲያድሩ ወስነዋል፡፡ የበዓሉ አከባበር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየሰፋና አድማሱ ብሔራዊነትን እየያዘ መጣ፡፡

 

ከዐፄ ገብረ መስቀል ጀምሮ የአደባባይ በዓል የሆነው የጥምቀት በዓል በ15ኛው ክ/ዘመን በደገኛው ኢትዮጵያዊው ንጉሠ ነገሥት ዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ(1426-1460 ዓ.ም)  አማካኝነት ታቦታቱ ወደ ወንዝ ወርደው ዕለቱን እንዳይመለሱ፣ በዚያ ፈንታ በጥምቀት ዋዜማ ጥር 10 ቀን ከሰዓት በኋላ ወደ ባሕረ ጥምቀቱ ወርደው እንዲያድሩ፣ አገሩን በኪደተ እግር ይባርኩም ዘንድ በሄዱበት መንገድ እንዳይመለሱ በዐዋጅ ወሰኑ፡፡ ይህን ታሪክ በመከተል ዐፄ ናዖድ (1486-1500) ዓ.ም) ማንኛውም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ምእመን ታቦተ ሕጉ ወደ ባሕረ ጥምቀቱ በሚወርድበት እና ከባሕረ ጥምቀቱ ወደ ቤተ መቅደሱ በሚመለስበት ጊዜ አጅቦ አውርዶ፣ አጅቦ መመለስ እንዳለበት በዐዋጅ አስነግረው ነበር፡፡ ሕዝቡም ታቦታተ ሕጉን በሆታና በእልልታ ከቤተ መቅደስ አጅቦ ከአወጣ በኋላ በባሕረ ጥምቀት ከትሞ ማደር ጀመረ ።/ሐመር ጥር/የካቲት 1998 ዓ.ም/

 

ketera 3ታቦታት ከአንድ በላይ ሆነው ወደ ከተራው ስለሚሄዱ እግዚአብሔር አምላክ ለነብዩ ሙሴ “የታቦት መኖር ከእናንተ ጋር የመኖሬ ምልክት ነው” ዘፀ 25÷1 እንዳለው ታቦተ ሕጉን ተሸክመው ዮርዳኖስን እንደ ተሻገሩት ካህናተ ኦሪት፤ ካህናቱ የማይለወጠውን ታቦተ ሕጉን በራሳቸው ተሸክመው የብሉዩን ሥርዓት ከሐዲስ ኪዳን ጋር አንድ አድርገው የሐዲስ ኪዳን መሠረት ኢየሱስ ክርስቶስን እያሰቡ፤  ካህናተ ሐዲስም ወደ ከተራ (ዮርዳኖስ) ይጓዛሉ፡፡ ሊቃውንቱም እንዲሁ ለበዓሉ የሚስማማውን ቃለ እግዚአብሔር እያደረሱ እንደሚያድሩ ሊቀ ጠበብት ሐረገወይን አገዘ ያስረዳሉ።

 

ሊቀ ጠበብት አያይዘውም የከተራ ዕለት ጥር 10 ቀን ኢየሱስ ክርስቶስ በዮሐንስ እጅ ለመጠመቅ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ የሄደበትን ለማዘከር ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ኃዳፌ ነፍስ ለጻድቃን የሚለውን ዋዜማ ይቆማሉ፡፡  የዋዜማው ቀለም  ከቀኑ በአራት ሰዓት በመላው አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ይጀመራል ከዚያም የዋዜማው ሥርዐት ቅዱስ ተብሎ እስከ ሰላም ያለው ቀለም ይደርሳል፡፡ በዕለቱም ቅዳሴ ይቀደሳል፡፡ ታቦተ ሕጉን የሚያነሡት ሰሞነኛ ካህን ከምግበ ሥጋ ተከልክለው ለዕለቱ የሚገባውን ጸሎት ያደርሳሉ፡፡

 

በከተራው ዕለት ድንኳን ተተክሎ፣ ዳሱ ተጥሎና ውኃው ተከትሮ ሁሉም ነገር ከተስተካከለ በኋላ ታቦተ ሕጉ የሚንቀሳቀስበት ሰዓት ሲደርስ የየቤተ መቅደሱ ታቦታት  በወርቅና በብር መጎናጸፊያ እየተሸፈኑ በተለያየ ኅብር በተሸለሙ የክህነት አልባሳት በደመቁ ካህናትና የመጾር መስቀል በያዙ ዲያቆናት ከብረው፣ ከቤተ መቅደስ ወደ አብሕርት /ምጥማቃት/ ለመሄድ ሲነሡ መላው አብያተ ክርስቲያናት የደወል ድምፅ ያሰማሉ፡፡ ምእመናን ከልጅ እስከ ዐዋቂ በዐጸደ ቤተ ክርስቲንና ታቦታቱ በሚያልፉባቸው መንገዶች ‘’ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ …’’ እንደሚባለው ያማረ ልብሳቸውን ለብሰው በዓሉን ያደምቃሉ፡፡

 

ሊቀ ጠበብት የበዓሉን ሂደት ሲገልጹ ታቦቱ ከመንበረ ክብሩ ሲነœ ‹‹ዮም ፍስሀ ኮነ›› ተብሎ ከተጸነጸለ በኋላ ታቦቱ ወጥቶ ወረደ ወልድ እምሰማያት ውስተ ምጥማቃት የሚለው ሰላም በሊቃውንቱ  ይዘመራል፣ ይጸነጸላል፣ ይመላለሳል፡፡ የወርቅ ካባና ላንቃ የለበሱ ቀሳውስት፣ መነኮሳት ጥላ የያዙት ከታቦቱ ጎን መስቀልና ጽና የያዙት ከታቦቱ ፊት ይሄዳሉ፡፡ እንደ ቀሳውስቱ ተመሳሳይ ልብሰ ተክህኖ የለበሱት ዲያቆናት ጥላ፣ መስቀልና ቃጭል ይዘው እያቃጨሉ ከቀሳውስቱ ፊት በመሆን ያጅቧቸዋል፡፡ ከነዚህም ሌላ ካባ፣ ላንቃ ጥንግ ድርብ የለበሱ መዘምራን የብር፣ የነሐስ መቋሚያና ጸናጽል ይዘው ‹‹ወረደ ወልድ›› የሚለውን አመላለስ እያሸበሸቡ ዲያቆናቱን ቀድመው ይሄዳሉ፡፡

 

የደብር አለቆችና አበው ካህናት ታቦቱን ተከትለው ይጓዛሉ፡፡ የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎችም በተለያዩ ቀለማት ባሸበረቁ አልባሳት ተውበው ትርዒት እያሳዩ “ወረደ ወልድ፣ እግዚኡ መርሐ፣ ሆረ ኢየሱስ” እና ሌሎችንም የአማርኛ መዝሙራትን እየዘመሩ፣ እናቶች “ነይ ነይ እምዬ ማርያም” እያሉ ሌሎችም ምስጋናዎችም እየቀረቡ ጉዞ በዝግታ ወደ ጥምቀተ ባሕር ይሆናል፡፡

 

የከተራ በዓል ማክበሪያ ቦታ እንደደረሱ ታቦታቱ በድንኳኑ አጠገብ ቆመው ‹‹ወረደ ወልድ›› የሚለው ሰላም ተመርቶ በአግባቡ ከተለዘበ በኋላ ጸሎት ተደርጎ የዕለቱ ትምህርተ ወንጌልና ዝማሬ  ከቀረበ በኋላ ውዳሴ ማርያም፣ መልክዐ ኢየሱስ ተደግሞ  ታቦታ ሕጉ  ወደ ተዘጋጀላቸው ድንኳን ይገባሉ /ሠርግው፤ 1981፣ 9/፡፡ በሁለተኛ የአገልግሎት ክፍል  ካህናቱ ስብሐተ እግዚአብሔር ሲያደርሱ ያድራሉ፡፡ በመንፈቀ ሌሊትም ሥርዐተ ቅዳሴው ተጀምሮ ከሌሊቱ በ9፡00 ሠርሆተ ሕዝብ ይሆናል፡፡ በነጋታው የሥርዐተ ጥምቀቱ መርሐ ግብር ይቀጥላል፡፡

 

የከተራ በዓል ምሳሌያት

በበዓለ ጥምቀት ዋዜማ የታቦታቱ ወደ ወንዝ መውረድና የባሕረ ጥምቀቱ መዘጋጀት  ሃይማኖታዊ ታሪክና ምሳሌ አለው፡፡የቃል ኪዳኑን ታቦት አክብሮ መጓዝና ወደ ወንዝ መወረድ የተጀመረው በአሮን ልጅ በአልዓዛር ጊዜ ነው፡፡ ኢያሱ በሙሴ እግር ተተክቶ ሕዝበ እስራኤልን እየመራ ከዮርዳኖስ ወንዝ ሲደርስ ባሕሩ ከሁለት ይከፈልና ወራጁም ይቆም/ይከተር/ ነበር፡፡ እስራኤል ዘሥጋ ወደ ምድረ ርስት ለመግባት የዮርዳኖስን ወንዝ ሲሻገሩ፡- ድንኳን ጥለው የቃል ኪዳኑን ታቦት በድንኳን ውስጥ አድርገው ሌዋውያኑ በዙሪያው፣ ካህናቱ ደግሞ በውስጥ ኾነው እግዚአብሔርን እያመሰገኑ አድረው በማለዳ ተሻግረዋል /ኢያሱ 3÷8-9/፡፡  ካህናቱ የቃል ኪዳኑን ታቦት አክብረው  የወንዙን ዳርቻ በረገጡት ጊዜ እንደ ክረምት ማዕበል ይወርድ የነበረው ውኃ ግራና ቀኝ ተከፍሎ እንደ ግድግዳ ወደ ላይ ቆሟል፡፡ ሕዝቡ ተሻግሮ እስከሚያበቃ ታቦተ ጽዮንን ያከበሩት  ካህናት ከወንዙ መሀል ይቆሙ ነበር፡፡ በዚህ መሠረት ‹‹ወተጠምቃ እገሪሆሙ ለካህናት›› ይህም ‹‹የካህናት እግሮቻቸው የዮርዳኖስን ውኃ በመርገጣቸው እንደ ጥምቀት ሆናቸው›› በሐዲስ ኪዳነ ጌታችን ለመሠረተው ሥርዐተ ጥምቀት ምሳሌ ነበር፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን የጥምቀትን ዋዜማ ከተራ ብላ የጠራችው ከዚህ በመነሣት ነው፡፡

 

ጌታችን በተጠመቀ  ጊዜ የዮርዳኖስ ወንዝ የላይኛው ሸሽቶ ወደ ላይ ተመልሶ ሽቅብ ፈሷል፡፡ የታቹም ወደ ታች ሸሽቷል፡፡ የላይኛው ፈሳሽ ተቋርጦ እንደ ክምር ተቆልሎ ቀርቷል።ቅዱስ ዳዊት የተመለከተውም ይህንኑ ነው። ከአዳም ጀምሮ እስከ ክርስቶስ ድረስ በዘር ይወርድ የነበረው ፍዳ መርገም በክርስቶስ ቤዛነት ተቋርጦ ፤ የታቹም ፈጽሞ መድረቁ ኃጢአተ አዳም የመጥፋቱ ምሳሌ ነው፡፡ እስራኤል ፈለገ ዮርዳኖስን ተሻግረው ወደ ኢያሪኮ  መሔዳቸው ምእመናን በጥምቀት ከኃጢአት ቍራኝነት ተላቀው እግራቸውን ወደ ልምላሜ ገነት ወደ ዕረፍት መንግሥተ ሰማያት አቅንተው ለመሔዳቸው ምሳሌ ነው፡፡  ኢያሱ የጌታ፣ እስራኤል  የምእመናን፣ ዮርዳኖስ የጥምቀት፣ ምድረ ርስት የገነት መንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው፡፡

 

ታቦቱን አክብሮ  የሚሔደው ካህን የቅዱስ ዮሐንስ፣ታቦቱ የጌታችን፣  ባሕረ ጥምቀቱ የዮርዳኖስ ወንዝ፣ ታቦታቱን አጅበው የሚሔዱትና በዓሉን የሚያከብሩት ምእመናን ወደ ቅዱስ ዮሐንስ እየመጡ የንስሐ ጥምቀት ሲጠመቁ የነበሩት ሰዎች ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ታቦታቱ በጥምቀት ዋዜማ ከመንበራቸው ወደ ጥምቀተ ባሕር መውረዳቸውና በዚያ ማደራቸው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእደ ዮሐንስ በፈለገ ዮርዳኖስ ከማታው ጀምሮ መውረዱንና ተሰልፎ ተራውን ሲጠብቅ ማደሩን ያጠይቃል፡፡ ‹‹ጥምቀት የሞቱና  የትንሣኤው ምሳሌ ነው፡፡ ከኃጥአን ጋር ተቆጥሮ እንዲጠመቅና እንዲሰቀል የተጻፈውን ቃል ንስሐና ጥምቀት የማያስፈልገው ሲሆን ነገር ግን  ፍጹም ኃጥእ መስሎ በዮሐንስ እጅ ጥምቀትን ለመፈጸም በማየ ዮርዳኖስ እግር ተጠመቀ፡፡›› /ኪ.ወ.ክ ፤517/፡፡

 

ጌታችን የተጠመቀበት ወርኀ ጥር በእስራኤላውያን ዘንድ የዝናብ፣ የበረዶ ወራት ነው፡፡ ከወንዝ ዳር ያለ መጠለያ መዋልና ማደር አይቻልም፡፡ በመኾኑም ከዮሐንስ ለመጠመቅ የሚሄዱ ሰዎች ሁሉ በዮርዳኖስ ዙሪያ ድንኳናቸውን ተክለው ያርፉ ነበር፡፡ በዚህ አንጻር ዛሬም በባሕረ ጥምቀት ዙሪያ ድንኳኖች ዳሶች ይጣላሉ፡፡

 

በሀገራችን በተለያዩ አካባቢዎች በተለይ በአክሱም የንግሥት ሳባ መዋኛን ‹‹ማይ ሹም›› በጎንደር የዐፄ ፋሲል መዋኛን፣ በላስታ የላሊበላ መዋኛን፣ በሸዋ የዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ፍርድ መስጫ አደባባይን፣ አርባ አራት ታቦታት የሚያድሩበትን የሸንኮራ ሜዳን “ራቡቴ ወንዝ” በአዲስ አበባ ደግሞ ጃንሆይ ሜዳን /ጃንሜዳን/ ወዘተ ለአብሕርተ ምጥማቃት እንደ ምሳሌ መጥቀስ ይቻላል፡፡ እኒህ ቦታዎች ዛሬም ድረስ ተከብረው ይገኛሉ፡፡እኛ በዚህ ወቅት ታቦት ይዘን፣ ከወንዝ ወርደን፣ ድንኳን ተክለን በማክበራችን ይፈጸማል፡፡

ሐመር 19ኛ ዓመት ቁጥር 9 ጥር 2004 ዓ.ም.

የደብረ ምጥማቅ ጻድቃኔ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሕንፃ ግንባታ በመፋጠን ላይ መሆኑ ተገለጸ

ጥር 8 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

tsadekana 2 1በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት የምትገኘው ታሪካዊቷና ተአምረኛዋ የደብረ ምጥማቅ የጻድቃኔ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን እሰከ 25 ሚሊዮን ብር በሚደርስ ወጪ የቤተ ክርስቲያኑን ሕንፃ እየተገነባ መሆኑን  በአዲስ አበባ የተቋቋመው የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴ ገለጸ፡፡

ደብረ ምጥማቅ  የጻድቃኔ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያንን በዘመናዊ መልክ ለመገንባት እንዲቻል አዲስ አበባ ቦሌ አካባቢ በሚገኘው ደሳለኝ ሆቴል ታኅሣሥ  21 ቀን 2005 ዓ.ም. ከምሽቱ 12፡00 ሰዓት ጀምሮ የገቢ ማሰባበሰቢያና የምክክር መርሐ ግብር የተዘጋጀ ሲሆን በመርሐ ግብሩ ላይ ብፁዕ አቡነ ሰላማ የማእከላዊ ትግራይ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተገኝተዋል፡፡ ብፁዕነታቸው መርሐ ግብሩን በጸሎት ከከፈቱ በኋላ በሰጡት ቃለ ምዕዳን “የዚህ ታላቅና ታሪካዊ ቤተ ክርስቲያን ግንባታ ላይ መሣተፍ ባለ ታሪክ ከማድረጉም ባሻገር የቀደሙ ነገሥታትን አርዓያ መከተል ነው፡፡ በዚህም መሠረት ቤተ ክርስቲያኑን ተባብረን እንድንሠራውና የታሪኩ ተካፋይ እንድንሆን ከእኛ ይጠበቃል” ብለዋል፡፡

የደብረ ምጥማቅ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያንና የጻድቃኔ ቅድስት ማርያም መካነ ቅዱሳን አንድነት ገዳም አስተዳዳሪ መልአከ ምሕረት ቆሞስ አባ ፊሊጶስ አባተ “ምእመናን ወደ ገዳማችን እየመጡ ጸበሉን እየተጠመቁና እየጠጡ፤ እምነት እየተቀቡ፤ በጸሎት እየተጉ ድኅነትን ያገኛሉ፡፡ ገዳሙ ታላቅ የበረከት ቦታ ነው፡፡ ይህንን የቤተ ክርስቲያን ሥራ ምእመናን አቅማቸውን የፈቀደላቸው ያህል በገንዘብ፤ በጥሬ እቃ አቅርቦት፤ በጉልበትም ሆነ በእውቀታቸው እንዲራዱንና የበረከቱ ተሳታፊ እንዲሆኑ እንጠይቃለን“ በማለት ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

tsadekana 2 2በአዲስ አበባ የቤተ ክርስቲያኑ ሕንፃ አሠሪ ኮሚቴ ሰብሳቢ ኢንጂነር አማረ አበበ ባቀረቡት ሪፖርትም ቤተ ክርስቲያኑ ከተሠራ ረጅም ዘመናትን ማስቆጠሩ፤ ጣሪያው ማፍሰሱ፤ በደርግ ዘመነ መንግሥት በነበረው ጦርነት አደጋ ስለደርሰበት፤ እንዲሁም ከተለያዩ የአገራችን አካባቢዎች የሚመጡ ምእመናን ቁጥር ከፍተኛ መሆኑና ቤተ ክርስቲያኑ በመጥበቡ ምክንያት በአዲስ  መልክ ለመገንባት ታስቦ ወደ ሥራ ለመግባት እንደቻሉ ገልጸዋል፡፡ በዚህም መሠረት የቤተ ክርስቲያኑ የመሠረት ሥራ ተጠናቆ ወደ ዋናው ግንባታ የተገባና ሥራውን በተቀላጠፈ ሁኔታ ለማከናወን እንዲቻል የምክክር መርሐ ግብር እንደተዘጋጀ ገልጸዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ከሦስት መቶ በላይ ጥሪ የተደረገላቸው ምእመናን የተገኙ ሲሆን በቤተ ክርስቲያኑ ታሪክ ላይ ያተኮረ ዶክመንተሪ ፊልም ቀርቧል፡፡ ጥሪ ለተደረገላቸው ምእመናንም የእራት ግብዣ ተደርጎላቸዋል፡፡ በመጨረሻም ምእመናን የቃል ኪዳን ሰነድ ሞልተው  ከ1ሚሊዮን በላይ በጥሬ ብር፤ እንዲሁም በጥሬ እቃዎች አቅርቦት ቃል ኪዳን እንደተገባ ሰነድ ለማሰባበሰብ መቻሉን ከኮሚቴው አባላት ለማወቅ ተችሏል፡፡

በአማራ ክልል በሰሜን ሸዋ ዞን ሞጃና ወደራ ወረዳ ሰላ ድንጋይ የሚገኘው የደብረ ምጥማቅ ማርያምና የጻድቃኔ ቅድስት ማርያም መካነ  ቅዱሳን አንድነት ገዳም በ15ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በንጉሥ ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ አማካይነት እንደተመሠረተ የታሪክ ድርሳናት ያስረዳሉ፡፡ ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ቤተ ክርስቲያኑን ሊያሠሩ የቻሉበት ዋነኛ ምክንያትም፤ በግብፅ ሀገር ሃይማኖት፤ ዘር፤ ቀለም ሳትለይ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስትገለጽ የነበረችበት ቤተ ክርስቲያን እሰላሞች በማቃጠላቸው እጅግ አዝነው ስለነበር በኢትዮጵያ ውስጥ ሰሜን ሸዋ ላይ ቤተ ክርስቲያኑን እንዳሠሩ የታሪክ መዛግብት ያስረዳሉ፡፡

በንጉሥ ዘርዐ ያዕቀብ የተመሠረተው ይህ ገዳም አሁንም ባለንበት ዘመን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በሕልም፤ በራዕይና በተከስቶ እየተገለጸች ምእመናንን እየተራዳች፤ በስሟ ከፈለቀው ጸበል እየጠጡና እየተጠመቁ ከተለያዩ ደዌያት በመፈወስ ላይ ናቸው፡፡

የቤተ ክርስቲያኑን ሕንፃ ሥራ መርዳት ለሚፈልጉ ሁሉ በስልክ ቁጥር 0911243678፤ 0911207804፤ 0911616880፤ ደውለው ማነጋገር የሚችሉ ሲሆን በተጨማሪም ለሕንፃው ሥራ መፋጠን በባንክ መርዳት ለሚፈልጉ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አራት ኪሎ ቅርንጫፍ የደብረ ምጥማቅ ጻድቃኔ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሕንፃ አሠሪ ኮሚቴ በባንክ ቁጥር 1000033548625 መላክ እንደሚቻል ኮሚቴው አሳስቧል፡፡

ብፁዓን ገባርያነ ሰላም

ጥር 3 ቀን 2005 ዓ.ም.


በፍጡርና በፈጣሪ፤ በፍጡርና በፍጡር መካከል ችግሮችና አለመግባባቶች መፈጠራቸው የዚህ ዓለም ባሕርያዊ ግብር ነው፡፡ በተለይም የሰው ልጅ አለመግባባቶችን ዕለታዊ ባሕርዩ ወደ ማድረግ የደረሰም ይመስላል፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትም የእነዚህን ችግሮች ክሡትነት መጠቆማቸውም የሚሰወር አይደለም፡፡

 

አስቀድመን እንደገለጽነው ሰው በሰብአዊነቱ ከራሱ ጋር፣ ከፈጣሪው ጋርና ከሌሎቹም ሥነ ፍጥረታት ጋር የሚያጋጩት ብዙ ምክንያቶች አሉ፡፡ ከዚህም የተነሣ “ለምን ግጭት ተከሠተ” ብሎ መሞገት ጊዜ መጨረስ ሲሆን “ለምን አልታረቅሁም” ብሎ ራስን መጠየቅ ግን አግባብ ነው፡፡ ምክንያቱም የዕርቀ ሰላም መንገዶች እንደ ግጭቱ መንገድ የተንዛዙ ሳይሆኑ የተቆጠሩና የተሰፈሩ የተለኩ ሃይማኖታዊ እሴቶች ናቸውና፡፡

እነዚህ የተለኩ እሴታዊ የዕርቀ ሰላም መንገዶች ከየትኛውም አቅጣጫ ሊጀምሩ ይችላሉ፡፡ ምንም እንኳን ይቅርታ መጠየቅ ከአዳም ቢጀመርም የዕርቁ ሂደት የተጀመረው ግን ከእግዚአብሔር ነው፡፡ በፈራጅነቱ የሚታወቀው እግዚአብሔር በቸርነቱ፣ በከሃሊነቱና በምሕረቱ ሰውን ሊታረቅ ፈቃዱ ሆኗልና፡፡

 

በዚህ መልኩ የሚመሩ የዕርቀ ሰላም ጉዞዎች ሁለት ነገር ያስፈልጋቸዋል እንላለን፡፡ የመጀመሪያው ሁሉንም ነገር ስለ እግዚአብሔር ብሎ ያለ አንዳች ቅድመ ሁኔታና ስሌት ወይም ድርድር ይቅር ማለት ነው፡፡ “ይቅር ለእግዚአብሔር” የሚለው ኀይለ ቃል ዐረፍተ ነገሩ እንደማጠሩ ሳይሆን ሃይማኖታዊ ውሳኔን የሚጠይቅ የታላላቅ ሰዎች መገለጫም ነው፡፡

 

እንደሰማይ ከዋክብት እንደ ምድር አሸዋዎች የበዙ የግጭት ምክንያቶችን ሁሉ ስለ እግዚአብሔር ወይም ስለ ማምነው ፈጣሪ ስል ትቼዋለሁ ብሎ ወደ ዕርቀ ሰላም ዐደባባይ መዝለቅ የመንፈሳውያን ሰዎች ቁርጠኛ ውሳኔ መሆኑን መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡

 

ሁለተኛው ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነት፣ ለምንኖርባት ምድር በጎነት፣ ለምእመን ፍቅር ስንል “ይቅር ለእግዚአብሔር” ማለት በእጅጉ ይገባናል፡፡ ይህን ማድረግ በራሱ የቸር እረኛነት ማሳያ መነጽር ነው፡፡ ይህን ስንል በግጭትና በጭቅጭቅ ከሚገኝ ትርፍ ይልቅ በይቅርታና በሰላም የሚያጋጥም ኪሣራ/ ካለም/ የበለጠ ትርፋማ መሆኑን ስለምናምን የበለጠም መንፈሳዊ ፍሬ እንደሚገኝ ለሁላችንም ግልጽ ነው፡፡

 

እንደነዚህ ዓይነቶችን የዕርቀ ሰላም ማውረጃ መንፈሳዊ እሴቶች ወደ ጎን በመግፋታችን አንዲቷ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከተፈጥሮአዊ ባሕርይዋ ውጭ ተከፈለች መባሉ በራሱ አንገት አስደፊ መርዶ ነው፡፡

 

ከዚህ አኳያ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በብዙ ምክንያቶች ላለፉት ሁለት ዐሥርት ዓመታት በአንድነቷ፣ በአገልግሎቷ፣ በሥርዐቷና በቀኖናዋ ላይ ጥቂት የማይባሉ ችግሮቹ በዚሁ እንዲቀጥሉ ከፈቀድንላቸው አሁን ከምንገኝበት የበለጠና የከፋ ችግር ተሸክመው ሊመጡ እንደሚችሉ መገመቱን ቀላል ያደርገዋል፡፡

 

በተለይም ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን “ስደተኛ ሲኖዶስ” እና “የአገር ቤቱ ሲኖዶስ” በማለት የነገር ብልት ለሚያወጡ አፅራረ ቤተ ክርስቲያን ጀርባዋን ለግርፋት አመቻችታ እንድትሰጥ ማድረግ ነውና ዕርቀ ሰላሙን ማስቀደም የሁላችንም ተግባር ሊሆን ያስፈልጋል፡፡ እንዲህ መሆኑ ደግሞ በመንፈሳዊነትና በአሳታፊነት እናከናውነዋለን ለምንለው የፓትርያርክ ምርጫውም ሆነ ለተቋማዊ ለውጥ የተመቻቸና የተሻለ መንገድ እንደሚሆን እናምናለን፡፡

 

በይበልጥ ጉዳዩ የሚመለከታቸው ብፁዓን አበው የአንድነቱን ሁለንተናዊ ጥቅም በመመልከትና የዕርቀ ሰላሙ ድርድር ውጤት አልባነት ክትያዎች በምእመኑ መካከል የሚያስከትሉትን ጉዳቶች በማስተዋል ለዕርቀ ሰላሙ ቅድሚያ ሊሰጡ ይገባል፡፡

 

አንድ ቦታ ላይ አቁመን የትናንቱን የውዝግብ አጀንዳ እንዝጋው፡፡ መቃቃርና መገፋፋት በተጠናወተው መንፈስ ስለትናንት ጥፋት ብቻ መነጋገር አቁመን ስለ ነገም የቤተ ክርስቲያን ዕድገት እንምከር፡፡ ትናንት በታሪክ አጋጣሚ ብንቀያየምም ዛሬ ግን በዕርቀ ሰላም በአንድነት መጓዝ እንችላለን፡፡ ይህም ሊሆን የሚችለው ነገ ዛሬ ሳንል በጨዋነትና በግልጽ ተወያይተን፣ ችግሮቻችንን ለይተን ስለ ሰላም ይቅር ስንባባል ብቻ መሆኑን ከአባቶቻችን ይሰወራል ብለን አናምንም፡፡

 

ከይቅርታና ከይቅር ባይነት የበለጠ ነገር በቅዱሳት መጻሕፍትም ሆነ በቤተ ክርስቲያናችን ትውፊት ስለሌሉና ስለማይኖሩ ለዕርቀ ሰላሙ ድርድር ውጤታማነት ትኩረት ሰጥተው ቢሠሩበት እንላለን፡፡

 

ማኅበረ ካህናትና ማኅበረ ምእመናንም እስከአሁን እየተከናወነ ያለውን በጎ ተግባር በመደገፍ ለወደፊቱም ለቤተ ክርስቲያናችንና ለምእመናን አንድነትና ሰላም በጸሎት መበርታት ይገባናል፡፡ የተጀመረው የዕርቀ ሰላም ድርድር ከውጤት እንዲደርስ የድርሻቸውን እያበረከቱ የሚገኙ በሁለቱም በኩል ያሉትን ተደራዳሪ አባቶች፣ አደራዳሪ ሽማግሌዎችና የተለያዩ ግለሰቦችን በምንችለው ሁሉ ልንደግፋቸው ይገባል፡፡

 

በወንጌል እንደተጻፈው ሰላምን የሚያደርጉ ብፁዓን፣ ንዑዳን ናቸው መባሉ ሁላችንንም የሚመለከት የበጎ ተግባር ምስክርነት ስለሆነ ለዕርቀ ሰላሙ ድርድር ውጤታማነት የድርሻችንን ልንወጣ ያስፈልሪጋል እንላለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

  • ምንጭ፡- ጽምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት ቁ.8 2005 ዓ.ም.
abunehizkiel

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ለዕርቀ ሰላሙ ቅድሚያ ሰጥቶ እንደሚመክር ታወቀ

ጥር 3 ቀን 2005 ዓ.ም.

 

abunehizkielየቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ጥር 6 ቀን 2005 ዓ.ም. የሚካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ ለዕርቀ ሰላሙ ቅድሚያ ሰጥቶ እንደሚመክር የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊ፣ የደቡብና ምዕራብ አዲስ አበባ አህጉረ ስብከትና የከፋ ሸካ ቤንች ማጂ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል በተለይ ለስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ገለጹ፡፡

 

ለዕርቀ ሰላሙ ድርድር ወደ አሜሪካ የተላኩት አባቶች ተልእኳቸውን ፈጽመው በሰላም ወደ አገራቸው መመለሳቸውን ያስታወሱት ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል የተላኩት አባቶች በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ውሳኔ በመሆኑ እነዚሁ አባቶች በዕርቀ ሰላም ድርድር ወቅት የደረሱበትን የውሳኔ አሳብና ተያያዥ ጉዳዮች ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ጥር 6 ቀን 2005 ዓ.ም. በሪፓርት መልክ እንደሚያቀርቡ ገልጸዋል፡፡

 

ቅዱስ ሲኖዶስ ለዕርቀ ሰላሙ ቅድሚያ እንደሚሰጥና ለውጤታማነቱ እየሠራ መሆኑን የሚገልጹት ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል ዕርቀ ሰላሙ እንዲወርድ በራችንን ከፍተን እየጠበቅን ነው፡፡ በውጭ ያሉ አባቶችም ወደ አገራቸው በሰላም ገብተው ከእኛው ጋር አንድ ሆነው በፓትርያርክ ምርጫው በመራጭነትም ሆነ በተወዳዳሪነት ሊሳተፉ ይችላሉ ብለዋል፡፡

 

የፓትርያርክ ምርጫን ከዕርቀ ሰላሙ ጎን ለጎን ለማካሄድ የታሰበው ቤተ ክርስቲያኒቱ ያለ አባት፣ ምእመኑም ያለ እረኛ ተበትነው እንዳይቀሩ እንደሆነ የሚገልጹት ብፁዕነታቸው እኛም ለመንጋችን እናስባለን እንራራለን፡፡ አንድነትም እናመጣለን፡፡ ምእመኑ ተለያይቶ እንዳይቀርና በአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጥላ ሥር እንዲሆን መለያየትን ለማስወገድ እንጥራለን ብለዋል፡፡

 

ዋናው ቁም ነገር ዕርቀ ሰላም ነው የሚሉት ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል ለስኬታማነቱ በሽምግልናው ሂደት የአገር ሽማግሌዎችና ታዋቂ ሰዎች ተጨምረውበት የዕርቀ ሰላሙ ድርድር እንደሚቀጥል አስታውቀዋል፡፡

 

ከዚሁ ጋር አያይዘው የፓትርያርክ ምርጫ ደንብ መጽደቁን የሚገልጹት ብፁዕነታቸው ሥልጣኑ የምልዐተ ጉባኤው ስለሆነ በተጠራው አስቸኳይ ስብሰባ ዳግም ሊታይ እንደሚችል ገልጸዋል፡፡

 

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ 20ኛ ዓመት ቁጥር 8፣ 2005 ዓ.ም.
christmas 1

ጥበብ ዘየዓቢ እምነ ኩሉ ጥበብ ከጥበብ ሁሉ የሚበልጥ ጥበብ

ጥር 1 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን እሱባለው

christmas 1

ከሰማይ በታች ባሉት ፍጥረታት ላይ በገዢነት የተሾመው የዕለተ ዓርብ ፍጥረት የሰው ልጅ በምክረ ከይሲ ተታልሎ ከፈቃደ እግዚአብሔር ፈቀቅ በማለቱ ሞትን ወደ ዓለም አስገብቷል፡፡ በዚህም የተሰጠውን ነጻነት በገዛ ፈቃዱ አሳልፎ ሰጠ በምትኩም ወደ ሰይጣን ምርኮኝነት እና ጽኑ አገዛዙ ፈጽሞ ሄደ፡፡

 

መፍቀሬ ሰብእ አምላካችንም እንደ ወጣን እንቀር ዘንድ ተቅበዝባዦች እንድንሆንም አልወደደም፤ ባማረ በተወደደ ቸርነቱ ጎበኘን እንጂ፡፡ ወኢኃደጎሙ ውስተ ኃጕል ለዝሉፉ በዕደ ሰይጣን – በሰይጣን እጅ እንደተያዙ ሊቀሩ  በጥፋት ውስጥ አልተዋቸውም እንዲል፡፡ ከነበርንበት ጉስቁልና ያድነን ዘንድ የሰይጣን ምክሩን ያፈረሰው በአምላክነቱ፣ በከሃሊነቱ፣ ከጌትነቱ ወገን በምንም በምን ድል አልነሣውም ወኢሞኦ በኃይሉ መዋኢት ወኢኃየሎ በክሂሎቱ ወኢበምንትኒ እምዕበዩ አላ በትሕትናሁ ወፍትሐ ጽድቁ በትሩፋተ ምሥጢር እንግዳ- እንግዳ በሚሆን ተዋርዶ(ትሕትና) በሠራው ሥራ ድል ነሣው እንጂ፡፡

ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ አዳምንና ሔዋንን ለማሳት በእባብ ሥጋ ተሠውሮ የሞት ምክርን በመምከር ምክንያተ ስህተት ቢሆንም የክብር ባለቤት መድኃኒታችን ግን በልዩ ጥበቡ የጠላትን ምክር ያጠፋ ዘንድ አምላክም ሰው ሆነ በዚህም ከነበርንበት ውድቀት አነሣን፣ የጎሰቆለ ባሕሪያችንን አደሰልን አዲስ የሕይወት መንገድን ከፈተልን፡፡ ሰይጣን በእባብ ሥጋ ሲሰወር  ከአዳም ተሰውሮበት እንደ ነበረ ሁሉ የቃል ሥጋ መሆንም ከሰይጣን ዕውቀት በላይ ነበር፡፡ ሊቃውንት ይህንን ሲያብራሩ አምላክ እርሱ ባወቀ ጥበቡ ጽንሰቱንና ልደቱን ከሰይጣን ባይሰውር ኖሮ ጌታን አገኛለሁ በማለት በሄሮድስ አድሮ የገሊላን ሕጻናት እንዳስፈጀው ቀድሞ በርካታ ጽንሶችን ባጨናገፈ ነበር፡፡ የሰውን ነገድ ሊያድን ወድዶ በሰማያዊ ቤቱ ካሉ መላእክት ተሠውሮ በድንግል ማኅጸን ተወሰነ፤ሥልጣኑን የሚቃወሙ አጋንንትን ባለማወቅ ሰወራቸው (እንዳያውቁ አደረገ) እንዲል ትምህርተ ኅቡዓት፡፡

ይህን የአምላክ ሰው መሆን በተመለከተ ሊቃውንት ሲናገሩ “እግዚአብሔር ዓለምን ከፈጠረበት ጥበቡ ይልቅ ሰው ሆኖ እኛን ያዳነበት ጥበቡ ይበልጣል(እጅግ ይደንቃል) ይላሉ፡፡ እንደ አምላክነቱ ፍጥረታትን መፍጠር የባሕርይ ገንዘቡ ናት፤ ነገር ግን አምላክ ከብቻዋ ከኃጢአት በስተቀር ሰው ሆኖ የቤዛነት ሥራ መሥራት ከኅሊናት ሁሉ  በላይ የሆነ ነገር በመሆኑ ከጥበብ ሁሉ የሚበልጥ ጥበብ ተብሏል፡፡ በዚህ ልዩ የጥበብ ጉዞ ውስጥ ኁልቈ መሣፍርት የሌላቸው ልብን የሚነኩ ምድራውያን ፍጥረታት በምንሆን በእኛ እውቀት የማይመረመሩ የጌትነቱን ሥራ እና ትሕትና ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ በቅዱስ በዝርዝር ጽፎት እናገኛለን፡፡/ሉቃ.2/

የማኅበራዊ ሳይንስ ሊቃውንት የሰው ልጅ ፍላጎት ወሰን ገደብ የለውም /Human needs are unlimited/ ሲሉ ይደመጣሉ፤ታዲያ ይህን  ወሰን አልባ መሻቱን እንኳ በገቢር በመሻት እንኳ አያረካውም ፡፡ ዘውትር አንድ የሚጎድለው ነገር እንዳለ ይሰማዋል ይህንንም ለማሟላት ጊዜውና አቅሙ የፈቀደለትን ነገሮች ሁሉ በማድረግ ይጠመዳል፡፡ ከማይገደቡ ፍላጎቶች መካከል ክብርን ዝናን መፈለግ ይገኙበታል፡፡ ክብርና ዝናን የማይሻ ሰው ካለ፥ እርሱ እግዚአብሔር ረድቶት፣ ባሕርያት ተስማምተውለት፥ ራሱን በፈጣሪው ፊት ባዶ ያደረገ ትሁት ሰው ነው፡፡ ከዚህ ውጭ በርካቶች በዚህ ጾር ተወግተው እንደ ወደቁ ቅዱስ መጽሐፍ ይመሰክራል፡፡ ሕንጻና ልጆች ስምን ያስጠራሉ  በማለት ክብርን ሲሹ ውርደትን የተጎናጸፉ ናምሩዳውያን/ባቢሎናውያንን  ማስታወስ ይችላል ዘፍ፲፩፥፩-፭ ይመለከቷል፡፡

አውግስጦስ ቄሳርም እንዲህ ባለ መሻት ተጠምዶ ስሙ በታሪክ መዝገብ ውስጥ በጉልህ ይጻፍለት ዘንድ  በግዛቱ ውስጥ ያሉ ሰዎች ሁሉ ይቆጠሩ ዘንድ ትእዛዝ አስተላለፈ፡፡ ትእዛዙም ከሚፈጸሙባቸው የሮማ ግዛት መካከል በገሊላ አውራጃ የምትገኘው የናዝሬት ከተማ አንዷ ነበረች ፡፡በአይሁድ ባሕል እንደ ተለመደው በየነገዳቸው ይቆጠሩ ዘንድ ሁሉም ነገዶች ወደ ዳዊት ከተማ ይተሙ ነበር፡፡ ወደ ከተማዋ ለቆጠራ ከወጡት መካከል ወንጌላዊው ለይቶ ሲናገር …ዮሴፍም ደግሞ ከዳዊት ቤትና ወገን ስለ ነበር ከገሊላ ከናዝሬት ከተማ ተነሥቶ ቤተልሔም ወደ ምትባል ወደ ዳዊት ከተማ ወደ ይሁዳ ፀንሳ ከነበረች ከእጮኛው ከማርያም ጋር ይጻፍ ዘንድ ወጣ፡፡ ሉቃ ፪፥፬-፮፡፡ ብሏል፡፡

 

እኛን በሕይወት መዝገብ ይጽፈን ዘንድ ወደዚህ ዓለም የመጣው ፍጥረቱ ጋር የነገሥታት ንጉሥ ኢየሱስ ክርስቶስ አውግስጦስ ቄሣር ባዘጋጀው መዝገብ ለመመዝገብ /ለመቆጠር/ ከእናቱ ጋር ወጣ፡፡ሉቃ ፲፥፳፣ ፊሊጵ ፬፥፫ ይመለከቷል፡፡

አዋጁ ለአረጋዊው ቅዱስ ዮሴፍ ከባድ ነበር በእርግና ዕድሜ ላይ ነበርና መውጣት መውረዱ እንዲህ በቀላል የሚወጣው ተግባር አልነበረም፡፡ በተጨማሪም የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም የመውለጃ ጊዜዋ ተቃርቧል፣ ይህ በእንዲህ እንዳለ ያንን ረጅም ጉዞ በድካም አጠናቅቀው ወደ ከተማዋ ሲገቡ ጠንከር ያሉት ተመዝጋቢዎች ቀድመው በመድረስ ከተማዋን አጣብበዋታል፡፡ የዳዊት ከተማም የዳዊትን ልጅ የምታስተናግድበት ሥፍራ አልነበራትም፡፡ ሉቃ ፪፥፭-፯፡፡

ጌታችን የዳዊት ከተማ በተባለች ቤተልሔም የተወለደው ያለምክንያትና  በአጋጣሚ አልነበረም፡፡ እርሱ ባወቀ አስቀድሞ ምሳሌውን አስመስሎ ትንቢቱን አስነግሮ ቆይቷል እንጂ፡፡ ይህም ሊታወቅ “አንቺ ቤተ ልሔም ኤፍራታ ሆይ አንቺ በይሁዳ አእላፋት መካከል ትሆኚ ዘንድ ታናሽ ነሽ ከአንቺ ግን አወጣጡ ከቀድሞ ጀምሮ ከዘላለም የሆነ በእስራኤልም ላይ ገዥ የሚሆን ይወጣልኛል፡፡” የሚለው የነቢዩ ሚኪያስ ቃለ ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ነው፡፡ ሚክ 5፥2 ከ4ቱ ዐበይት ነቢያት አንዱ የሆነ ነቢዩ ኢሳይያስም በትንቢቱ 1፥3 በሬ የገዢውን አህያም የጌታውን ጋጣ አወቀ እስራኤል ግን አላወቀም፡፡ በማለት በመንፈሰ እግዚአብሔር እንደተናገረ፣ እረኛና ሰብሳቢ ይሆነው ዘንድ የአብ ልጅ የማርያም ልጅ  ሥጋን ይዋኻድ ዘንድ ወደዚህ ዓለም መጣ፡፡

 

ይህን የወልድን ትሕትና ስናስብ ፍጻሜ ወደሌለው አግራሞት ይመራናል፡፡ ከግሩማን ፍጥረታት ይልቅ ግሩም የሆነ ገናናነቱ፣ ተቆጥረው የማያልቁ ብዙ የብዙ ብዙ የሚሆኑ ትጉሃን መላእክት የሚያመሰግኑት ፈጣሪ እንደ ምስኪን ድሃ በግርግም መወለዱን ስናስብ ዕፁብ ዕፁብ ብሎ ከማድነቅ የበለጠ ምን ቋንቋ ሊኖረን ይችላል?

መጠንና መመርመር በሌላት ፍቅሩ ስለወደደን በከብቶች ግርግም ተወለደ፣ ጒስቈልናችንን  ያርቅልን ዘንድ ስለ እኛ ጒሰቈለ፤ መርገማችንን አስወገደ ፡፡ ዘፍ ፫፥፲፮፡፡ ሰው መሆን ቢያቅተን ሰው ሆኖ ያድነን ዘንድ ወደደ ተወልደ “በአምሳሊከ ከመ ይለድከ በአምሳሊሁ-በራሱ አምሳል ይወልድህ  አንተን መስሎ ተወለደ” እንዳለው፡፡  አረጋዊ መንፈሳዊ፡፡

ከአበው አንዱ ይህን ሲተረጉም፡- ወደ ሰማያት ከፍ ከፍ ያደርገን ዘንድ፥ ከሰማያት ወረደ፤ ወደ ምስዋዕ(መሰውያ) ከፍ ከፍ ያደርገን ዘንድ በበረት ተወለደ፤ ለራሱ ከበረት በቀር ሌላ ማደሪያ ሳያዘጋጅ፥ ለእኛ በአባቱ ዘንድ ብዙ ማደሪያን ያዘጋጅ ዘንድ፥ ከልዕልና ወደ ትሕትና ወረደ” ብሏል፡፡ ዮሐ፲፬፥፪፡፡

በሰዎች ዘንድ ማደሪያን ቢፈልግ አላገኘም፤ ግእዛን የሌላቸው እንስሳት ግን ያላቸውን አልነፈጉትም፡፡ ቅዱስ ያሬድ እንዳለው እስትንፋሳቸውን በመገበር ጌታቸውን እንዳወቁ መሰከሩ፡፡ የነቢዩ የኢሳይያስ ትንቢትም ተፈጸመ፡፡ኢሳ ፩፥፫ በሬ የገዢውን አህያም የጌታውን ጋጣ አወቀ እስራኤል ግን አላወቀም፡፡ ማደሪያዎቹ የሆን እኛ ሰውነታችንን ምን ያህል ለእርሱ አዘጋጅተን ይሆን ወይስ እንደ ዳዊት ከተማ በእንግዶች ብዛት ሥፍራ ነሥተነው ይሆን? በመጽሐፍ ልጄ ሆይ ልብህን ስጠኝ እንደ ተባለ ልባችንን መስጠት ያስፈልገናል፡፡ ከደጅ ቆሞ ሲያንኳኳ በራችንን የከፈትንለት ስንቶቻችን ነን?

ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲወለድ  በነገሥታት፣ በሠራዊቱ እና በጻሕፍት ዘንድ ማደሪያን እንዳላገኘ፣  በዚያም እንዳላደረ፥ ዓለምና ፈቃዷ በሚናኝበት ሰው ዘንድም እንዲሁ ሥፍራ ስለማይኖረው በዚያ አያድርም፡፡ ይልቁንም …የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቃል አባቴም ይወደዋል ወደ እርሱም እንመጣለን በእርሱም ዘንድ መኖሪያ እንደርጋለን፡፡ ዮሐ ፲፬፥፳፫ ፡፡ እንዳለው ልደቱን ስናስብና  በዓሉንም ስናከብር የእግዚአብሔር ማደሪያ ለመሆን መሠራት ይጠበቅብናል፡፡.. “መንፈሳዊ ቤት ለመሆን ተሠሩ፡፡” እንዲል ፩ጴጥ ፪፥፭፡፡

ልደቱንም ወዲያው ንጉሡ እና ሠራዊቱ  እንዲሁም ኦሪትንና ነቢያትን ጠንቅቀን እናውቃለን ይሉ የነበሩት ጸሐፍት ፈሪሳውያን ሌሎቹም ወገኖች በሙሉ ይህንን ታላቅ የምስራች ለመስማት አልበቁም፡፡ ዓለም እንዲህ ባለ ዝምታ ታላቁን  የነገሥታት ንጉሥ ተቀበለች፡፡ ሰማያውያን ቅዱሳን መላእክት ግን ዝምታን አልመረጡም፥ በብርሃን ጐርፍ ተጥለቅልቀው፣ በአንክሮ ተውጠው ምስጋናን ጀምሩ፡፡ ዓይናቸውን ወደ ሰማይ አቅንተው፥ ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሐርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ አንድነት ሳይለይ በግርግም በግእዘ ሕፃናት የተገለጠውን እግዚአብሔር ወልድን አይተው “ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት” በማለት አመሰገኑት ዳግመኛ ወደ ምድር ሲመለከቱ በእመቤታችን እቅፍ ሥጋን ተዋኽዶ አገኙት በዚህን ጊዜ እየሰገዱ “ወሰላም በምድር  ለዕጓለ እመሕያው” በማለት አመሰገኑት እንጂ፡፡ መንጋቸውን በትጋት በመጠበቅ ላይ ለነበሩት ኖሎትም ዓለም ያልተረዳውን እውነት አበሠሩ፡፡ ትጉኅ እና እውነተኛ እረኛ መድኀኔዓለም ልደቱን በበረት ገለጠላቸው፡፡

የተመሰገነ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ ከጥበብ ሁሉ የሚበልጠውን ይህን የአምላካችንን ጥበብ ለምን እንዲህ ባለ ሁኔታ እንደ ፈጸመው ሲገልጽ ሀብታም ሲሆን እናንተ በእርሱ ድህነት ባለጠጎች ትሆኑ ዘንድ ስለ እናንተ ድኃ ሆነ” ፪ቆሮ፰፥፱ ብሏል፡፡

መላእክት ቀድመው ትስብእቱን በደስታ እንዳበሰሩት አሁን ደግሞ ልደቱን በልዩ ደስታ አወጁ፡፡ ከዚያ በፊት በርካታ ነቢያት፣ካህናት፣ መሳፍንትና ነገሥታት ተወልደው ነበር፡፡ በእነዚህ ጊዜያት የተሰማ የምስጋና ቃል አልነበረም፤ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደ ጊዜ ግን ልዩ ቃለ ማኅሌት ተሰምቷል፡፡ ምክንያቱም የተወለደው ነቢያትና ካህናት ለሰው ልጆች ይሰጡ ዘንደ ያልተቻላቸውን ድኅነት ይሰጥ ዘንድ የመጣ እግዚአ ነቢያት/የነቢያት ጌታ/፣ ሰያሜ ካህናት/የካህናት ሿሚ/እና የነገሥታት ንጉሥ  በመሆኑ ልዩ ምስጋናን አቅርበዋል፡፡እግዚአብሔርን በሰማይ የሚተካከለው ማን ነው ከአማልክትስ ልጆች እግዚአብሔርን ማን ይመስለዋል? በቅዱሳን ምክር እግዚአብሔር ክቡር ነው፡፡ መዝ፹፰፥፮-፯ እንዲል፡፡

ጌታ በተወለደባት ሌሊት ታላቁን የደስታ ምስራች ከመላእክት በመስማት መንጋቸውን በትጋት በመጠበቅ ላይ ከነበሩት ኖሎት የቀደመ አልነበረም፡፡ በዚያም ምድር መንጋቸውን በሌሊት ሲጠብቁ በሜዳ ያደሩ እረኞች ነበሩ፡፡እነሆም የጌታ መልአክ ወደ እነርሱ ቀረበ የጌታ ክብርም በዙሪያቸው አበራ ታላቅ ፍርሃትም ፈሩ፡፡መልአኩም እንዲህ አላቸው እነሆ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምስራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋልና፡፡ይህም ምልክት ይሆንላችኋል፥ ሕፃን ተጠቅልሎ በግርግም ተኝቶ ታገኛላችሁ፡፡ድንገትም ብዙ የሰማይ ሠራዊት ከመልአኩ ጋር ነበሩ ፡፡እግዚአብሔርንም እያመሰገኑ ክብር ለእግዚአብሔር  በአርያም ይሁን፥ ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ አሉ፡፡ሉቃ፪፥፰-፲፬፡፡

እነዚህ እረኞች የሌሊቱ ግርማ ያላስፈራቸው ስለ መንጋቸው በትጋት የቆሙ፣የተሰጣቸውን ሓላፊነት ከመወጣት ቸል ያላሉ በመሆናቸው፥ የታማኝ አገልጋዮች ምሳሌ ናቸው፡፡መንጋውን በትጋት የሚጠብቁ እረኞች ሁሌም ዋጋቸው ከፍ ያለ ነው፡፡ ለዚህም ነው መልአኩ ዜና ልደቱን ለማብሠር ወደ ምኵራብ ወይም ወደ ንጉሡ ያልሄደው ይልቁንም ወደ ተጉት እረኞች ሄደ እንጂ፡፡

ሁላችንም ዛሬ እንደ እረኞቹ በቤተ ክርስቲያን የየራሳችን ድርሻ ይኖረናል፡፡ የእረኝነት ሓላፊነት የተሰጠን መንጋውን በመጠበቅ፣ የተቀረነው ደግሞ ከመንጋው አንዱ  እንደመሆናችን ራሳችንን  ለማስጠበቅ መዘጋጀት ይጠበቅብናል፡፡ እንዲህ ባለ ሁኔታ ስንታመን የደስታው ተካፋዮች እንሆናለን፡፡

እረኞቹ ከመላእክት ጋር አመሰገኑ፥ ዮም አሐደ መርዔተ ኮኑ መላእክት ወሰብእ ከመ ይሰብሕዎ ለክርስቶስ በቃለ አሚን፥ እነሆ በአንድ የምስጋና  ቃል ክርስቶስን ያመሰግኑ ዘንድ መላእክትና ሰዎች አንድ መንጋ ሆኑ፡፡” እንዳለ ቅዱስ ያሬድ፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም “እነሆ ቤተልሔም ጽርሐ አርያም ሆነች” በማለት ተናግሯል፡፡

ይህቺን ዕለት ያዩ ዘንድ ብዙ ነቢያት ሽተው፣ በትንቢታቸው በርካታ ነገርን ተናግረዋል ክንድህን ላክልን፣ ብርሃንህን ላክልን፣ ሰማዮችን ቀድደህ ምነው ብትወርድ እያሉ ተማጽነዋል፡፡ ሁሉም ነቢያት በአንድ መንፈስ ቅዱስ ስለ ክርስቶስ በትንቢት ቃል ተንብየዋል፡፡ይህ ሁሉ ትንቢት ሲከናወን እያንዳንዱን ነገር ትመለከት የነበረችው  የነቢያት ትንቢታቸው የተባለች፣ በሰው ልጅ የመዳን ሂደት(ነገረ ድኅነት) ውስጥ ምክንያተ ድኂን የሆነች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ግን ከጥበብ ሁሉ  በላይ የሆነውን ይህን የአምላክ ሰው ሆኖ መገለጥ ጥበብ በልቧ ትጠብቀው ነበር፡፡

በጾሙ እንደ ነቢያት የጌታን መወለድ ናፍቀናል፡፡ እኛ ግን ነቢያት ያላገኙትን ዕድል አግኝተናል፡፡ ይኸውም በዐይናችን ዐይተነዋል፣ በጆሮአችንም ሰምተነዋል፡፡ ስለዚህ ካየነው ከሰማነው ዘንዳ ሰውነታችንን ለእርሱ እንዲመች አድርገን ወደ ሕይወታችን እንዲመጣ ልንፈልግ፣ ልንፈቅድ ይገባናል፡፡ በቅዱስ ሥጋው በክቡር ደሙ ወደ ሕይወታችን ይገባልና፡፡

የሕይወታችን መሪ እርሱ ነውና፥ በዓለም ማዕበል ተነድተን ከጽድቅ ወደብ ሳንደርስ ወድቀን እንዳንጠፋ በእመቤታችን አማጅነት በቅዱሳን ሁሉ ቃል ኪዳን በልዩ ጥበቡ በጽድቅ ጎዳና እንዲመራን ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን

እነሆ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኀኒት ተወልዶላችኋል ሉቃ.2፥11

ታኅሣሥ 27 ቀን 2005 ዓ.ም.

መጋቤ ብሉይ አእምሮ ዘውዴ

እንኳን ለጌታችን ለመድኀኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፡፡


የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውኃ ፈሳሽ  አይደለም፡፡ ከጥንት ከመሠረት ጀምሮ በመላእክት፤ በነቢያት  ሲነገር፤ ሲሰበክ የመጣ ነው እንጂ፡፡ ማቴ.1፥18፡፡

 

ሰው የመሆኑን ምሥጢር ለመጀመሪያ ጊዜ በማእከለ ገነት የተናገረ እርሱ እግዚአብሔር ነው፡፡

yeledeteአባታችን አዳም ከእግዚአብሔር ትእዛዝ ወጥቶ ዕፀ በለስን በልቶ ከጸጋ እግዚአብሔር በተራቆተ ጊዜ /አዳም ኮነ ከመ አሐዱ እምኔነ/ አዳም ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ ዘፍ.3፥22 ብሎ ከሦስቱ ቅዱስ አንዱ ቅዱስ እግዚአብሔር ወልድ በተለየ አካሉ ከእመቤታችን ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ ሰው እንደሚሆን ተናግሯል፡፡ በዚህ ቃል መሠረት /መሪነት/ ቅዱሳን መላእክት ምሥጢረ ትንቢት ተገልጾላቸዋል፡፡ እነሱም የተገለጸላቸውን ምሥጢረ ትንቢት ኀላፍያትንና መጻእያትን ለሚናገሩ ነቢያት ነግረዋቸዋል፡፡ ቅዱሳን ነቢያትም ከእግዚአብሔር ያገኙትን ከመላእክት የሰሙትን መነሻ አድርገው በተለያዩ ጊዜያት በተለያዩ ምሳሌያት በተለያዩ ዘመናት የወልደ እግዚአብሔርን ሥጋዌ ሰብከዋል /ገልጸዋል/ ዕብ.1፥1፡፡ ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዓይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናግሮ፥ሁሉን ወራሽ ባደረገው ደግሞም ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ በዚህ ዘመን መጨረሻ ለእኛ ተናገረን፡፡

የጌታችን ልደት በትንቢተ ነቢያት

ከዓበይት ነቢያት መካከል አንዱ የሆነው ነብየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ የሚከተለውን ትንቢት ተናግሯል፡፡

እነሆ ድንግል በድንግልና ፀንሳ በድንግልና ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ትለዋለች ኢሳ.7፥14፣ ሕዝ.44፥1/ ፡፡ በኅቱም ድንግልና ተፀንሶ በኅቱም ድንግልና የተወልደው አማኑኤል ጌታ ነው፡፡ ትርጉሙም  እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ሆነ ማለት ነው፡፡ነቢዩ  በጎላና በተረዳ ነገር “ሕፃን ተወልዶልናል ወልድም ተሰጥቶናል አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፡ ስሙም ድንቅ መካር ኀያል አምላክ የዘለዓለም አባት የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል“ በማለት የሚወለደው ሕፃን የባሕርይ አምላክ የዘለዓለም አባት የሰላም አለቃ ሥልጣን የባሕርይ ገንዘቡ እንደሆነ እና ለሥልጣኑም ወሰን ድንበር እንደሌለው ተናግሯል፡፡

 

ከደቂቀ ነቢያት መካከል አንዱ ሚክያስም በቤተልሔም ስለመወለዱ፡-

  • የኤፍራታ ምድር አንቺ ቤተልሔም ከይሁዳ አለቆች ከቶ አታንሽም ሕዝቤን እስራኤልን የሚጠብቅ ንጉሥ ከአንቺ ይወጣልና ሚክ.5፥2፣ ማቴ.2፥6/ ብሏል፡፡

  • ነቢየ እግዚብሔር ቅዱስ ዳዊትም እነሆ በኤፍራታ ሰማነው ዛፍ በበዛበትም ቦታ አገኘነው እንግዲህስ ወደ እግዚአብሔር ማደሪዎች እንገባለን ብሎ የወመለዱን ምሥጢር ተናግሯል መዝ.131፥6

  • ነቢዩ ዕንባቆምም አቤቱ ድምፅህን ሰምቼ ፈራሁ ሥራህንም ዐይቼ አደነቅሁ በሁለት እንስሶች መካከል አየሁህ ዘመኑ እንደደረሰ አድርጌ አውቅህአለሁ ዘመኑም በደረሰ ጊዜ ተገለጥክ ብሎ በቤተልሔም በረት በተወለደ ጊዜ አድግና ላኅም እስትንፋሳቸውን እንደሚገብሩለት ዕንባቆም 3፥1 ተናግሯል፡፡

 

christmas 1ከዚህ በኋላ የዘመኑ ፍጻሜ ሲደርስ እግዚአብሔር መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልን ወደ ድንግል ማርያም በመላክ አብሥሯታል፡፡ “ማርያም ሆይ፥ በእግዚአብሔር ፊት ጸጋ አግኝተሻልና አትፍሪ። እነሆም፥ ትፀንሻለሽ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፥ ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ።እርሱ ታላቅ ይሆናል የልዑል ልጅም ይባላል፥ ጌታ አምላክም የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል” በማለት፡፡ ሉቃ. 1፡32

 

እመቤታችንም በብዙ ኅብረ አምሳል ትንቢት ሲነገርለት፤ ምሳሌ ሲመሰልለት፤ ሱባኤ ሲቆጠርለት የነበረውን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በቤተልሔም ግርግም /ዋሻ/ ወለደችው፡፡

 

ይህንንም ብስራት በቤተልሔም ዋሻ መንጋቸውን ነቅተውና ተግተው ይጠብቁ ለነበሩ እረኞች መጋቤ ሐዲስ አብሣሬ ትስብዕት ቅዱስ ገብርኤል ፤ እነሆ ዛሬ መድኀኒት በዳዊት ከተማ ተወልዶላችኋል ይኸውም ቡሩክ መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የሚያርቅ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ የሚያድል ከዓለም በፊት ንጉሥ የነበረ ዛሬም ከዳዊት ባሕርይ /ዘር/ በቤተልሔም ዋሻ ዓለምን ለማዳን የተወለደ የዳዊት ልጅ ንጉሠ ነገሥት ኢየሱስ ክርስቶስ ተወለደ ሲል አበሰራቸው፡፡ መዝ.73፥12

 

የጌታችንን ልደት ስናነሣ ሁለት ልደታት እንዳሉት እናምናለን፡፡ እኒሁም ልደታት /ልደት ቀደሚዊና/ /ልደት ደኃራዊ/ ናቸው፡፡

ልደት ቀዳማዊ፡ ቅድመ ዓለም ከአብ አካል ዘእም አካል ባሕርይ ዘእም ባሕርይ ከእግዚአብሔር አብ ያለ እናት የተወለደው ልደት ሲሆን /ነቢዩ ዳዊት እንዲህ ይገልጸዋል፡፡ ወለድኩከ እምከርሥ እምቅድመ ኮከበ ጽ    ባህ መዝ.109፥3 ከአጥቢያ ኮከብ አስቀድሞ ወለድኩህ ፤አንተ ልጄ ነህ እኔም ዛሬ ወለድኩህ መዝ.2፥7

 

ልደት ደኃራዊ ፤ አምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ሲፈፀም በሀሙስ ዕለት ወበመንፈቃ ለዕለት እትወለድ እምወለተ ወለትከ እንዲል ቃሉ፡፡ ቅድስት ድንግል ከምትሆን ከእመቤታችን እንበለ ዘርዓ ብዕሲ ያለ አባት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቤተልሔም የተወለደው ልደት ነው፡፡

 

ቀዳማዊ ልደቱ ጥንትና ፍጻሜ የሌለው የማይመረመር ስለሆነ ቀዳማዊ ልደቱን ለመግለፅ ቅድመ ዓለም ያለ እናት ከአብ እንደ ተወለደ ድኅረ ዓለምም ከእመቤታችን /እንበለ ዘርዓ ብዕሲ/ ያለ አባት ተወለደ፡፡ እሱም እመቤታችን ያለ አባት የወለደችው ፤ እግዚአብሔርም ያለ እናት የወለደው ወልድ ዋሕድ ኢየሱስ ክርስቶስ

 

በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ሰባቱ መስተጻርራን /ተቃራኒ ነገሮች አንድ ሆነዋል

ሕዝብና አሕዛብ፤ በጠብና በክርክር ይፈላለጉ የነበሩ ሕዝብና አሕዛብ በጌታችን ልደት ታርቀዋል፡፡ ይኸውም ሊታወቅ ከዚህ አስቀድሞ ቤተ መቅደሱን ለማፍረስ ንዋየ ቅድሳቱን ለመዝረፍ ሕዝቡን ለመማረክ ምታ ነገሪት ብለው ይመጡ የነበሩ  የሩቅ ምስራቅ /የፋርስ የባቢሎን ሰዎች በጌታችን ልደት ምክንያት ወርቅ፣ ዕጣን፣ ከርቤ አይቴ ሀሎ ዘተወልደ ንጉሠ አይሁድ የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው ማቴ.2፥4 እያሉ መጥተው ወርቅ፣ እጣን፣ ከርቤ ገብረውለታል፡፡

 

ነፍስና ሥጋ፡- በሲዖልና በመቃብር ተለያይተው የነበሩ ነፍስና ሥጋ ከእመቤታችን ከነፍሷ ነፍስ ከሥጋዋ ሥጋ ነሥቶ በተዋሕዶ ሰው በሆነ ጊዜ ነፍስና ሥጋን አስታርቋል፡፡

 

ሰውና እግዚአብሔር፡- አባታችን አዳም አትብላ የተባለውን ዕፀ በለስ በልቶ የሰውና የእግዚአብሔር የፍቅር ግንኙነት ለአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ተቋርጦ ነበርና ጌታችን የሰውን ሥጋ ተዋሕዶ በተወለደ ጊዜ እርቀ ሰላም ተገኝቷል፡፡

 

ሰውና መላእክት፡- አባታችን አዳም ከእግዚአብሔር ጋር በተጣላ ጊዜ ቅዱሳን መላእክትም ስለተጣሉት በምትገለባበጥ ሰይፈ እሳት አስፈራርተው ከገነት ከአስወጡት በኋላ ወደ ገነትም እንዳይገባ ገነትን ይጠብቁ ነበር፡፡ ጌታችን በተወለደ ጊዜ አንድ ሆነው ዝማሬ አቅርበዋል፡፡ ይኸውም ዮም አሐደ መርኤተ ኮኑ መላእክት ወሰብእ ከመ ይሰብህዎ ለክርስቶስ እንዲል፡፡ ሰውና መላእክት ክርስቶስን ለማመስገን አንድ ሆኑ  እንዳለ ሊቁ፡፡

 

ቤተ ክርስቲያን ጌታችን የተወለደባት እና ሰባቱ መስተጻርራን አንድ የሆኑባት፤ ሰውና መላእክት የዘመሩባት የብርሃን ጎርፍ የጎረፈባት እንስሳት እስትንፋሳቸውን የገበሩባት ቤተልሔም በቤተ ክርስቲያን ትመሰላለች፡፡

 

ቤተልሔም፡- ተለያይተው የነበሩ ሕዝብና አሕዛብ ፤ሰውና እግዚአብሔር፤ ነፍስና ሥጋ ፤ሰውና መላእክት አንድ ሆነው በቤተልሔም እንደዘመሩ ዛሬም የፍቅር ተምሳሌትና የአማኞች ሁሉ እናት በሆነችው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በዘር፣ በጎሣ፣ በጥቅም፣ በሥልጣን ሳንከፋፈል አንዲት ቤተ ክርስቲያንን በፍቅር እንድናገለግል በቤተልሔም የተደረገው የልደቱ ምሥጢር ይህን ያስተምረናል፡፡

ክርስቲያኖች የጌታን መወለድ የምናስበው በዚህ መንፈስ ነው፡፡

abune_nathnael

ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የእንኳን አደረሳችሁ መልእክት አስተላለፉ፡፡

ታኅሣሥ 26 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


abune_nathnaelየኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል ምክንያት በማድረግ ባስተላለፉት መልእክት “በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ፣ ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትኖሩ የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ በሕመም ምክንያት በየሆስፒታሉ ያላችሁ እንዲሁም የሕግ ታሪሚዎች ሆናችሁ በማረሚያ ቤት የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት እንኳን ለ2005 ዓ.ም. የጌታችን የአምላካችንና የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዐለ ልደት በሰላም አደረሳችሁ፡፡” ካሉ በኋላ “በጌታችን ቤዛነት እንድን ዘንድ አንድ ልጁን ወደ ዓለም ልኮአልና፤ እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን ፍቅር በዚህ አውቀናል፡፡ እግዚአብሔር ከፍጡራን ሁሉ የተለየና ከአእምሮ በላይ የሆነ መለኮታዊ ኀይል ያለው አምላክ በመሆኑ የባሕርዩን ጥልቅነት በምልአት ማወቅ ፈጽሞ የማይቻል ቢሆንም እርሱ ራሱ በገለጸልን መጠን የተወሰኑ ነገሮችን እናውቃለን፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ “እግዚአብሔር ፍቅር ነው” ብሎ ምልአተ ፍቅሩን ካስረደ በኋላ በማስረጃ ሲያብራራ ቤዛ ሆኖ የሰውን ልጅ ያድን ዘንድ አንድ ልጁን ወደ ዓለም ልኮአልና ፍቅሩን በዚህ አውቀናል” ይላል፡፡ እግዚአብሔር በልጁ መሥዋዕትነት ዓለምን ለማዳን ያደረገው ፍቅር ከሌላው ሁሉ የበለጠ በመሆኑ ልቆ ተነገረ እንጂ የእግዚአብሔር ፍቅር ከፍጡራን የተለየበት ጊዜ እንደሌለ ሁላችንም እናውቃለን፤ በስፋትም ልንገነዘብ ይገባልና፡፡” ብለዋል፡፡
ብፁዕ አቡነ ናትናኤል እግዚአብሔር ለፍጥረቱ በፍቅር ከሰጣቸው ስጦታዎች ሁሉ በቤተልሔም ለዓለም ስለሰጠው ስጦታ ሲናገሩ “የቤተልሔም ስጦታ ከስጦታዎች ሁሉ እጅግ በጣም የላቀ ነው፡፡ ምክንያቱም ሌሎች ስጦታዎች ከፍጥረቶቹ የሚገኙ የፍጥረት ውጤት ስጦታዎች ሲሆኑ የቤተልሔም ስጦታ ግን አንድ ልጁን ነውና” ብለዋል፡፡ ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል በማጠቃለያ መልእክታቸው “እግዚአብሔር እኛን ይህን ያህል ከወደደን እኛም እርስ በርሳችን ልንዋደድ ይገባናል፤ ከልደተ ክርስቶስ የምንማረው ትምህርት ወገንን ሁሉ ማለትም በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠረውን የሰው ዘር ሁሉ መውደድና መርዳት ነው፡፡… ባለንበት ዘመን በተለያየ ምክንያት እናትና አባትን ያጡ፣ የወገንን ፍቅርና እንክብካቤ የሚሹ ብዙ የእግዚአብሔር ልጆች በየሠፈሩ አሉ፡፡ ለበዐል መዋያ ያዘጋጀነውን ኅብስተ በረከት ከተቸገሩት ሕፃናትና የሚላስ የሚቀመስ ካጡ ወገኖች ጋር በመሆን በኅብረት መመገብ ይገባናል፡፡ ይህን ስናደርግ በፍጹም ፍቅሩ የወደደንን እግዚአብሔርን በቤታችን ውስጥ እየጋበዝን እንደሆነ እርግጠኞች መሆን አለብን፡፡ “ተርቤ አብልታችሁኛልና ኑ ወደ እኔ” የሚል ቃል ኪዳን እንዳለበትም እናስታውስ፡፡” ብለዋል፡፡
christmas 1

የሕፃኑ የኢየሱስ ልደት /ለሕፃናት/

ታኅሣሥ 26 ቀን 2005 ዓ.ም.

ከወልደ ኢየሱስ /ቤካ ፋንታ/

  • “እነሆ ድንግል ትፀንሳለች ልጅም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ትለዋለች” ማቴ.1፥23

 

ልጆችዬ እንደምን ሰነበታችሁ? ዛሬ ስለ ታላቁ ሕፃን ልደት የምነግራችሁ ነገር አለና በማስተዋል ተከታተሉኝ እሺ፡፡ ጎበዞች!

christmas 1

የዛሬ ሁለት ሺ ዓመት ገደማ ነው፡፡ በኢየሩሳሌም ሀገር ንጉሡ ሄሮድስ ሕዝቡን ሁሉ ቤተልሄም ወደምትባል ከተማ ጠራቸው፡፡ እመቤታችንም በዚያ ጊዜ የአሥራ አምስት/15/ ዓመት ልጅ ሆኖ በሚጠብቃት በአረጋዊው /በሽማግሌው/ ዮሴፍ ቤት ትኖር ነበር፡፡ እመቤታችን ድንግል ማርያም ሕፃኑን ኢየሱስ ክርስቶስን ፀንሳ ልትወልድ ደርሳ ሳለ ወደ ቤተልሄም ከተማ ከአረጋዊው ጠባቂዋ ዮሴፍና ከቅድስት ሰሎሜ ጋር ሄደች፡፡

 

በዚያ ሲደርሱ ምን ሆነ መሰላችሁ? እናታችን ማርያም ቅድስት ሰሎሜና አረጋዊው ዮሴፍ ማደሪያ ፈልገው በየቤቱ እየሄዱ “የእግዚአብሔር እንግዶች ነን ማደሪያ ስጡን፣ እባካችሁ አሳድሩን…” ብለው ቢጠይቋቸው ሁሉም “ቦታ የለንም፣ አናሳድርም፣ አናስገባም ሂዱ፡፡” እያሉ መለሷቸው፡፡ በጣም መሽቶ ስለነበረ ጨለማው ያስፈራ ነበረ፣ ብርዱ ደግሞ በጣም ከባድ ነበረ፡፡ ማደሪያ አጥተው የት እንሂድ እያሉ ሲያስቡ በድንገት አረጋዊ ዮሴፍ “ኑ ተከተሉኝ” ብሎ በመንደሩ ውስጥ ወዳለ አንድ የከብቶች ማደሪያ ቤት ወሰዳቸው፡፡

 

ከከብቶቹ ቤት ሲደርሱ በዚያ አህዮች፣ በሬዎች፣ በጎች፣…. ብዙ እንስሳት ተኝተው አገኙዋቸው፡፡ የበረቱ ሽታ በጣም ያስቸግር ነበረ፡፡ ነገር ግን ማደሪያ ስላልነበረ በዚያ ሊያድሩ ተስማሙ፡፡

 

ወደ በረቱ ሲገቡ እንስሶቹ ከተኙበት ተነሥተው በደስታ እየዘለሉ ተቀበሏቸው፡፡ በዚያም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሕፃኑን ኢየሱስ ክርስቶስን ወለደችው፡፡ ይህም ታላቅ ሕፃን የሁላችንም አምላክ ነው፡፡ ወዲያውኑ የከብቶቹ ቤት በታላቅ ብርሃን ተሞላ፡፡ ቅዱሳን መላእክት ተገለጡ፤ በእመቤታችንም ፊት ሆነው በደስታ ከበሮ እየመቱ፣ እያጨበጨቡ መዘመር ጀመሩ፡፡ መዝሙሩም እንዲህ የሚል ነበር፡-

 

“ለእግዚአብሔር ክብርና ምስጋና በሰማያት ይሁን፣ በምድርም ሰላም ለሰውም በጎ ፈቃድ”


ልጆችዬ አሁን አንድ ጥያቄ ልጠይቃችሁ ነው፡፡ ተዘጋጃችሁ? መልካም፡-

  • የገናን በዓል እንዴት ነው የምታከብሩት? ለሕፃኑ ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት መዝሙር እየዘመርን ነው አላችሁኝ? ጎበዞች! የገናን በዓል ከወላጆቻችሁ ጋር በቤተ ክርስቲያን ተገኝታችሁ እንደ ቅዱሳን መላእክት በደስታ መዝሙር በመዘመር አክብሩት እሺ፡፡

መልካም የገና በዓል ይሁንላችሁ፡፡

st. tekela

“ወብዙኀን ይትፌሥሑ በልደቱ በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል” ሉቃ.1፥14

ታኅሣሥ 25 ቀን 2005 ዓ.ም.

ዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

st. tekela

  • በዘመነ ብሉይ የእግዚአብሔር ድምፅና የመልአክ ብሥራት ብርቅ በነበረበት ወቅት ካህኑ ዘካርያስና ቅድስት ኤልሳቤጥ ልጅ መውለድ አጥተው ባረጁበት ዘመን የእግዚአብሔር መልአክ ካህኑ ዘካርያስን እንዲህ አለው፡፡

መልአኩም እንዲህ አለው “ዘካርያስ ሆይ፥ አትፍራ፤ ጸሎትህ በእግዚአብሔር ፊት ተሰምቶአልና፤ ሚስትህ ኤልሣቤጥም ትፀንሳለች፤ ወንድ ልጅንም ትወልድልሃለች፤ ስሙንም ዮሐንስ ትለዋለህ፡፡ ደስታና ሐሤትም ይሆንልሃል፤ በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል፡፡ እርሱ በእግዚአብሔር ፊት ታላቅ ይሆናልና የወይን ጠጅና የሚያሰክርም መጠጥ ሁሉ አይጠጣም፤ ከእናቱ ማሕፀን ጀምሮም መንፈስ ቅዱስ ይመላበታል፡፡ ከእስራኤልም ልጆች ብዙዎችን ወደ አምላካቸው ወደ እግዚአብሔር ይመልሳቸዋል፡፡ እርሱም የአባቶችን ልብ ወደ ልጆች፥ የከሓድያንንም ዐሳብ ወደ ጻድቃን ዕውቀት ይመልስ ዘንድ፥ ሕዝብንም ለእግዚአብሔር የተዘጋጀ ያደርግ ዘንድ በኤልያስ መንፈስና ኀይል በፊቱ ይሄዳል፡፡”ሉቃ1፥13-18 ይህ ለመጥምቁ ዮሐንስ የተነገረ ቃል ቢሆንም ወላጆቹ (ካህኑ ዘካርያስና ቅድስት ኤልሳቤጥ) በእግዚአብሔር ፊት ጻድቃን እንደነበሩ በቅዱስ ወንጌል ተገልጿል /ሉቃ.1፥6-7/ እንደዚሁ ሁሉ ካህኑ ጸጋዘአብና ሚስቱ እግዚእ ሐረያ በእግዚአብሔር ሕግና ሥርዓት ይመሩ የነበሩ ደጋግ ክርስቲያኖች ነበሩ፡፡ ይህም ሊታወቅ በትሩፋት ሥራ፣ በጾም፣ በጸሎት፣ በምጽዋት የታወቁ ነበር፡፡ በተለይም የሊቀ መላእክት የቅዱስ ሚካኤል በዓልን ምክንያት በማድረግ ይመጸውቱ ነበር፡፡ የመልአኩም ጥበቃ ባለ ዘመናቸው ሁሉ አልተለያቸውም ነበር፡፡ ጌታችን በቅዱስ ወንጌል ላይ “መልካም ዛፍ ሁሉ መልካም ፍሬን ያፈራል፣” /ማቴ.7፥17/ እንዳለ፣ ለዓለም ሁሉ የወንጌልን ብርሃን የሚያበስር ሐዲስ ሐዋርያ በቅድስናና በክብሩ ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ሃያ አምስተኛ ሆኖ ያመሰገነውን ጻድቅ ወለዱ፡፡ በሰሜን ሸዋ ጽላልሽ ልዩ ስሙ ኢቲሳ በተባለ ቦታ የተወለዱት ጻድቁ ተክለ ሃይማኖት በ12ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተነሡና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ትምህርት ከየመን እስከ ኬንያ ከሶማሌ እስከ ሱዳን ድረስ የተስፋፋበትን ወርቃማ ዘመንን ያስገኙ ጻድቅ አባት ናቸው፡፡

“ነገርን ከሥሩ ውኃን ከጥሩ” እንዲሉ የጻድቁን ታሪክ በአጭሩ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡


ቅዱሳኑ በትሩፋት ሥራ የተጠመዱ ነበሩ

ልጅ አጥተው ሲያዝኑ ይኖሩ የነበሩት ካህኑ ፀጋ ዘአብና ቅድስት እግዚእ ሐረያ፣ በየወሩ የቅዱስ ሚካኤልን በዓል ያከብሩ ነበርና መጋቢት 12 ቀን የተራበን ሲያበሉ ሞቶሎሚ ንጉሠ ዳሞት ሀገራቸውን ወርሮ ከእነርሱ ደረሰ፡፡ ጸጋ ዘአብም እንደማይምራቸው አውቀው አንከርት ወደሚባለው ባሕር ሮጡ፡፡ ከሞተሎሚ ጭፍሮች አንዱ ተከተላቸው፣ የማይደርስባቸው ሲሆን ሰይፉን ሊወረውርባቸው ቃጣ፡፡ ሰይፉ ከእጁ ተጠቅልላ ቀረች፡፡ በሌላ እጁ ሁለተኛ ሊወረውር ቢቃጣ አሁንም ተጠቅልላ ቀረች፡፡ እሳቸውም እንዳልተዋቸው አይተው ዘለው ከባሕር ገቡ፡፡ ከባሕር ውስጥ ሆነው እንዲህ አያሉ ይጮሁ ጀመረ…” ኀይል የምትሆነኝ ቅዱስ ሚካኤል፣ አምባ መጠጊያ የምትሆነኝ ቅዱስ ሚካኤል፣ ኀይልህ ወዴት ነው? ከኃሊነትህ ወዴት ነው? ተአምራት ማድረግህ ወዴት ነው? እንሆ መሞቻዬ ደረሰ፡፡ ዛሬ የሽብር ቀን ነው፡፡ ዛሬ የመከራ ቀን ነው፡፡ ዛሬ ጥፋት ተፈርዶብኝ፡፡ በበዓልህ ደስ ሳታሰኘኝ ታሳዝነኛለህን? እያሉ ያለቅሱ ጀመረ፡፡ እስመ ለመላእክቲሁ ይኤዝዞሙ በእንቲአከ ከመ ኢትትዐቀፍ በዕብን፤ እግርከ በመንገድህ ሁሉ ይጠብቁህ ዘንድ መላእክቱን ስለ አንተ ያዛቸዋልና፣ እግርህ በድንጋይ እንዳትሰናከል በእጆቻቸውም ያነሡሃል፡፡ እንዲል /መዝ.90፥11/ ቅዱስ ሚካኤል በውስጥ ሆኖ ተቀብሏቸዋል፡፡ “ወባሕርኒ ኮነቶ ከመ ደብተራ ዘድለት ለማኅደር” ይላል ባሕርም እንደ ድንኳን ሆነላቸው “ኦ ፍቁርየ ጸጋ ዘአብ አስመ አነ አዐቅበከ በይነ ዘይወጽእ እምሐቁከ፤ ወዳጄ ጸጋ ዘአብ ሆይ፥ ከአብራክህ ስለሚከፈለው ቅዱስ እጠብቅሃለሁና አትፍራ” አላቸው፡፡ ከዚህ በኋላ በሦስተኛው ቀን አውጥቶ ቤተ ክርስቲያን አድርሷቸዋል፡፡

 

በሌላ በኩል በሞቶሎሚ ወታደሮች የተማረኩት እግዚእ ሐረያ ለንጉሡ ሚስት ሊያደርጓቸው፣ ከቤተ መንግሥቱ አገቧቸው፡፡ ቅድስት እግዚእ ሐረያ ግን “ጌታዬ ፈጣሪዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ስንፍናዬን ለምን ተመለከትክ፡፡ በንጹሕ ሆኖ የሚያገለግል ባሪያህ ጸጋ ዘአብን ለምን አላሰብከውም አንተን ለሚክዱ ኃጥአን ለሚሆኑ ጠላቶች አሳልፈህ ለምን ሰጠኸኝ ሕግህን ሥርዓትህን ከማያውቅ ከሚያጸይፍ ባሪያ ልጅ ትሰጠኝ ዘንድ ወደድክን? ከዚያም ከንጹሕ አገልጋይህም ቢሆን አንተን ደስ የማያሰኝ ልጅ ካለሆነ ማኅፀኔን ዝጋው እልሃለሁ፡፡ አቤቱ የትድግና ባለቤት ዛሬ በእኔ ላይ ትድግናህን ግለጽ” በማለት ያመለክቱ ነበር፡፡ ጠባቂ መልአካቸው፡- ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ተገልጦ ከሠራዊት ሞቶሎሚ በመንጠቅ በክንፉ ታቅፎ ከዳሞት ዞረሬ በሦስት ሰዓት አደረሳቸው፡፡ በመጋቢት ሃያ ሁለት ቀን ጸጋ ዘአብ ከቤተ መቅደስ ገብተው ሲያጥኑና ስለ እግዚእ ሐረያ ሲለምኑ፣ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ከቤተ መቅደስ አግብቶ ከዚያ ትቷቸው ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ ገድለ ተክለሃይማኖት ምዕ.12

 

በዚህ ሁኔታ በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በመልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነት ደግም የተገናኙት ሁለቱ ቅዱሳን /ጸጋ ዘአብና እግዚእ ሐረያ/ መጋቢት ሃያ አራት ቀን ከአብራካቸው የሚከፈለውን ጻድቁ ተክለሃይማኖትን ፀነሱ፡፡ እነሆም ታኅሣሥ 24 ቀን ቅዱስ አባታችን ተወለዱ፡፡

 

“ገድለ ተክለሃይማኖት” የተባለው መጽሐፍ አባታችን ተክለሃይማኖት በተፀነሱበት መጋቢት 24 ቀን ለእናትና አባታቸው እግዚአብሔር ራእይ እንዳሳያቸው ይገልፃል፡፡ ቅድስት እግዚእ ሐረያ ያዩት ራእይ “የብርሃን ምሰሶ ከቤታቸው ውስጥ ቁሞ የሞሶሶው ራስ ከሰማይ ደርሶ በዓለም ያሉ ሕዝብ ሁሉ ነገሥታቱም ጳጳሳቱም በዙሪያው ቁመው እኩሌቶቹም ይሰግዱለታል፤ እኩሌቱቹም እሱን ጥግ አድርገው ይቀመጣሉ፡፡ በሱም ላይ ብዙ አዕዋፍ ተቀምጠውበታል፡፡እኩሌቶቹ ነጫጮች፣ እኩሌቶቹም ቀያዮች፣ እኩሌቶቹ አመድ አመድ ይመስላሉ፡፡ ዝጉርጉርም ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ካህኑ ጸጋ ዘአብ ደግሞ በዚሁ ሌሊት ስላዩት ሕልም ለእግዚእ ሐረያ ሲነግሩ እንዲህ ብለዋል፡- “ከምንተኛበት አጎበር ሥር ፀሐይ ሲወጣ፥ስፍር ቁጥር የሌላቸው ብሩሃን ከዋክብት በክንፉ ላይ ተቀምጠው ለዓለሙ ሁሉ ሲያበሩ፣ ከብርሃኑም ብዛት የተነሣ ሀገሩ ሁሉ አበራ፡፡ ይህን ራእይ ዐይቼ ደንግጬ አለቀስኩ”

 

ከዚህ በኋላ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል የሁለቱንም ህልም ይተረጉሙላቸው ዘንድ ከእግዚአብሔር ተልኳል፡፡ በትርጓሜውም፡- “ከጸጋ ዘአብ ቤት ሲወጣ የታየው ፀሐይ ከአብራኩ የሚከፈለው ልጁ ተክለ ሃይማኖት ነው፡፡ በብርሃኑ ከምእመናን ላይ የኃጢአትን ጨለማ የሚያርቅ ይሆናል፤ በክንፉም ላይ ታዝለው፥የታዩት ከዋክብት በመንፈስ ቅዱስ በእርሱ ትምህርት ይወለዱ ዘንድ ያላቸው ልጆቹ ናቸው፡፡ የእግዚእ ሐረያ ሕልም ትርጉሙ እንዲህ ነው በቤታቸው የብርሃን ምሶሶ ቁሞ ራሱ ከሰማይ ደርሶ ያያቸው ልጅህ ነው፡፡ ነገሥታቱ ጳጳሳቱ ሲገዙለት ያየችውም በእውነት ነገሥታቱ ይሰግዱለታል፡፡ አሕዛብም ይገዙለታል፡፡ ለሁሉም መጠጊያ ይሆናል፡፡ ከነገሥታቱ በላይ ሆኖ ይኖራል፡፡ ተአምራቱ ከዛፍ ፍሬ ይበዛል ሥፍር ቁጥር የለውም፡፡ እንደሣዕረ ምድር ጸንቶ ይኖራል፡፡ ስሙም ለዘለዓለም ሲመሰገን ይኖራል፡፡ ሰማይ ከምድር በላይ እንደሆነ የሱም ስም አጠራሩ እንደሱ ካሉ ከቅዱሳን ምእመናን በላይ ሆኖ ይኖራል፡፡ የሕልማችሁ ትርጓሜ ይህ ነው፡፡” በማለት የሕልሙን ፍች አስታውቋቸዋል፡፡

 

በሚያስደንቅ ልዩ ልዩ ተአምራት በቅዱስ ሚካኤል ጥበቃና በእግዚአብሔር ቸርነት ከብዙ መከራ ተጠብቀው የኖሩት ሁለቱ ቅዱሳን ባልና ሚስት /ካህኑ ጸጋ ዘአብና ቅድስት እግዚእ ሐረያ/ ታኅሣሥ 24 ቀን ፃድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖትን ወለዱ፡፡

 

ከሠተ አፉሁ

ታኅሣሥ 26 ቀን /በተወለዱ ሦስተኛው ቀን/ በዕለተ ሰንበት ከጧቱ ሦስት ሰዓት ላይ እጆቻቸውን አንሥተው ወደ ሰማይ እየተመለከከቱ “አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ፤ ማለትም፦ ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ በባሕርይ በሕልውና አንድ የሚሆን አብ በአካል በስም ልዩ ነው፣ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ በባሕርይ በህልውና አንድ የሚሆን ወልድ በአካል በስም ልዩ ነው፣ በህልውና አንድ የሚሆን መንፈስ ቅዱስ በአካል በስም ልዩ ነው” በማለት ሰማያዊያን  መላእክት ምድራውያን ጻድቃን ፈጣሪን በሚያመሰግኑበት ሥርዓት ሆነው አመሰገኑ፡፡ እናትየው እግዚእ ሐረያ ግን ይህንን በልባቸው እያደነቁ “ልጄ ፍሥሐ ጽዮን ምን ትላለህ ይህ ቃል የአባትህ ሥራ ነው፡፡ ላንተ ግን የሚገባህ ጡት መጥባት ነው” በማለት ተናገሩ፡፡ ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ግን ክቡር ዳዊት “እም አፈ ደቂቅ ወሕፃናት አስትዳሎከ ስብሐት፡፡ በእንተ ጸላዒ ከመ ትንሥቶ ለጸላኢ ወለገፋዒ፤ ከሕፃናትና ከሚጠቡ ልጆች አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ ስለ ጠላትህ ጠላትንና ቂመኛን ለማጥፋት” በማለት የተናገረው ቃል ተፈጽሞላቸዋል፡፡ መዝ.8፥2

 

“በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል” ተብሎ በመጋቢ ሐዲስ በቅዱስ ገብርኤል የተነገረለት ዮሐንስ መጥምቅ /ሉቃ.1፥14/ ከእናት አባቱ አልፎ ብዙዎችን ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያገናኘ የደስታ ምንጭ የሆነ ነቢይም ሐዋርያም ነው፡፡ በጻድቁ አቡነ ተክለሃይማኖት መወለድም፣ ለጊዜው ልጅ ባለማግኘት ለብዙ ዓመታት ሲያዝኑ ለነበሩ ወላጆቻቸው ታላቅ የምሥራችና ደስታ ሆኗል፡፡በፍጻሜው ግን ፈጣሪያቸውን ባለማወቅ በአጋንንት አገዛዝ ሥር ወድቀው የነበሩ በብዙ መቶ ሺህ የሚቆጠሩ ሰዎች በጸሎታቸው ኀይልና ግሩም በሆነው ትምህርታቸው ብርሃን ኢየሱስ ክርስቶስን ከባሕርይ አባቱ ከእግዚአብሔር አብና፣ ከባሕርይ ሕይወቱ መንፈስ ቅዱስ ጋር በአንድነት አውቀው ተረድተው ለስሙ እንዲገዙ አድርገዋል፡፡

 

ነቢዩ ኤርሚያስን ፈጣሪያችን ልዑል እግዚአብሔር ከእናቱ ሆድ ጀምሮ ለቅድስና ለክብር በነቢይነት እንደጠራው በመጻሕፋችን ተገልጦአል፡፡ /ኤር.1፥5/ ጻድቁ አቡነ ተክለሃይማኖትም ለኢትዮጵያ ሰዎች ሐዋርያ ሆነው ያገለግሉ ዘንድ በባለቤቱ በመድኀኔዓለም በኢየሱስ ክርስቶስ አንደበት “እስመ ረሰይኩከ ሐዲስ ሐዋርያ፤ አዲስ ሐዋርያ አድርጌ ሾሜሃለሁ” ተብሎ የተነገረላቸው ናቸው፡፡ በዚህም በጌታችን ቃል “በእኔ የሚያምን እኔ የምሠራውን ሥራ እርሱም ይሠራል ከዚያም የሚበልጥ ይሠራል” /ዮሐ.14፥12/ ተብሎ በተነገረው ቃል መሠረት፤ በሰው ሰውኛ ሊደረጉ የማይችሉ ታላላቅ ተአምራትን በመፈጸም ኢ-አማንያንን ወደ ሃይማኖት መልሰዋል፡፡ ተጋድሏቸውን የመዘገበው መጽሐፍ /ገድለ ተክለ ሃይማኖት/ እንደተመዘገበው በዛፍ ላይ አድሮ ሲያሰግዳቸውና ሲያስመልካቸው የነበረ ጋኔኑን አዋርደው እርሱን ከኢትዮጵያ ምድር አርቀው በአምልኮተ ባዕድ የነበሩ ሰዎችን ወደ ቤተ ክርስቲያን ኅብረት ቀላቅለዋል፡፡

 

ባለብዙ ገድል ጻድቁ ተክለ ሃይማኖት “ዳግማዊ ዮሐንስ” የሚል ስያሜ የተሰጣቸው ሐዋርያ ናቸው፡፡ ዮሐንስ መጥምቁ በተፀነሰ ጊዜ የአባቱን አንደበት የዘጋ፣ ሲወለድ ደግሞ የአባቱን አንደበት ዳግመኛ የከፈተ ነው፡፡ (ሉቃ.1፥62-66) መምህር ወመገስጽ ዘኢያደሉ ለገድ የተባለለት፥ ዮሐንስ መጥምቁ ንጉሥ ሔሮድስን ሳይፈራና ሳያፍር የገሰጸ እንደሆነ ሁሉ፤ አባታችን ተክለ ሃይማኖትም  እንደ ሞቶሎሚ ያሉ ጣዖት አምላኪና አስመላኪ ነገሥታትና ኀያላንን ሳይፈራ የተጠራለትን አገልግሎት በጽኑ መታመን የፈጸመ ነው፡፡

 

ፈጣሪያችን ከጻድቁ አባታችን ከተክለሃይማኖት በረከት ረድኤት ያሳትፈን፡፡ አሜን