ht

ፍኖተ ሐመረ ጽድቅ ዐውደ ርዕይ ተከፈተ

ነሐሴ 24 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

ዐውደ ርዕዩ እሰከ ከነሐሴ 28 ቀን 2005 ዓ.ም. ይቆያል፡፡
የማኅበረ ቅዱሳን ኅትመትና የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ዋና ክፍልን የሃያ ዓመታት የአገልግሎት ጉዞ የሚያሳይ ፍኖተ ሐመረ ጽድቅ ዐውደ ርዕይ በማኅበሩ ሕንፃ ላይ ተከፈተ፡፡

ht
ፍኖጸተ ሐመረ ጽድቅ ዐውደ ርዕይ ነሐሴ 23 ቀን 2005 ዓ.ም. ከቀኑ 11፡00 ሰዓት ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የቦረና፤ አማሮና ቡርጂ አኅጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ ብፁዕ አቡነ ሰላማ የታዕካ ነገሥት ባዕታ ለማርያም ገዳምና የመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የበላይ ጠባቂ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችና አገልጋዮች በተገኙበት መርቀው ከፍተዋል፡፡

ht 2ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የቦረና አማሮና ቡርጂ አኅጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የሐመር መጽሔትና የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንና ምእመናን ያደረጉትን አስተዋጽኦ፤ እንዲሁም ከአመሠራረታቸው ጀምሮ የተጓዙበትን ሂደት በጥልቀት አብራርተዋል፡፡ በ1985 ዓ.ም. ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና የማኅበሩ አባላት በተገኙበት ውይይት በማካሔድ ሐመር መጽሔት ተብሎ እንዲሰየም ውሳኔ ላይ መደረሱን ተናግረዋል፡፡

ብፁዕነታቸው የኅትመት ውጤቶቹ እየሰጡ የሚገኙትን አገልግሎት ሲገልጹም “በሐመር መጽሔትና በስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ የሚጻፈው፤ የሚነበበው ነገረ ድኅነትን ያመለክታል፡፡ የምንድንበትን መንገድ የሚያስተምሩ፤ ፃድቃን ሰማዕታት አማላጅ መሆናቸውን የሚያውጁ፤ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ የሁሉ ጌታ፤ የሁሉ ፈጠሪ መሆኑን የሚመሰክሩ፤ እምነትንና ምግባርን የሚያስተምሩ ናቸው” ብለዋል፡፡

ምእመናንን በማነጽ ረገድም “ወደ ቤተ ክርስቲያን መጥተው የማያውቁ ወንድሞችና እኅቶች የኅትመት ውጤቶቹን በማንበብ ራሣቸውን በማረም እምነታቸውን እንዲያውቁና እንዲጸኑ አድርጓቸዋል፡፡ ከኢትዮጵያ አልፎም በዓለም ዐቀፍ ደረጃ እየተሰራጩ ምእመናንን በመታደግ ላይ ይገኛሉ፡፡ ይህም ታላቅ ሐዋርያዊ አገልግሎት ነው” በማለት ወደፊትም ተጠናክረው እንዲቀጥሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ht 3
የማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ የማኅበሩ የኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ለቤተ ክርስቲያንና ለምእመናን ያላቸውን ፋይዳ በማስመልከት “በሐመር መጽሔትና ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ የተጀመረው አገልግሎት እድገት በማሳየት ሌሎች የኅትመት ውጤቶችን በመውሰድ ምእመናንን በማስተማር ላይ ይገኛሉ፡፡ የዘመኑ ቴክኖሎጂ ውጤቶችንም በመጠቀም የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያው ዘርፍ በተለያዩ ቦታዎች ላይ በአንድ ጊዜ በመድረስ የተሻለ አገልግሎት መስጠት ያስችለዋል” ብለዋል፡፡

ዲያቆን ዶክተር መርሻ አለኸኝ የሚዲያ ዋና ክፍል ሓላፊ የዐውደ ርዕዩ አስፈላጊነት በሚመለከት “ዐውደ ርዕዩ የሐመር መጽሔትና የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ በሃያ ዓመታት ጉዞ ውስጥ ያሳዩአቸውን ጠንካራና ደካማ ጎን ለይተን እንድናውቅ፤ የኅትመትም ይሁን የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያው የአገልግሎት ዘርፍ የወደፊት አቅጣጫ እንድንተልም ይረዳናል” ብለዋል፡፡ በተጨማሪም በሚቀጥለው ወር በመንፈሳዊው ሚዲያ ዘርፍ ልምድ ባላቸው አንጋፋ ጋዜጠኞች አማካይነት በማኅበሩ የኅትመት ሚዲያ ላይ ዐውደ ጥናት እንደሚካሔድ ገልጸዋል፡፡

ht 4ዐውደ ርዕዩ አራት አበይት ክፍሎች ሲኖሩት ዝክረ ሐመረ ጽድቅ፤ መዛግብትና ቁሳቁስ፤ የፎግራፍና የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ዘርፍ እንቅስቃሴን ይዳስሳል፡፡ ዐውደ ርዕዩ እሰከ ነሐሴ 28 ቀን 2005 ዓ.ም. ድረስ የሚቆይ ሲሆን ምእመናን አራት ኪሎ በሚገኘው በማኅበሩ ሕንፃ ላይ ከጠዋቱ 4፤00 ሰዓት እስከ ምሽቱ 2፤00 ሰዓት ድረስ እንዲመለከቱ ተጋብዘዋል፡፡

የሰው ሰውነት ክፍሎች

ሐሴ 23 ቀን 2005 ዓ.ም. 

በመ/ርት ኖኀሚን ዋቅጅራ

ባለፈው ግእዝን ይማሩ አምዳችን ላይ የግእዝ ቁጥሮችን አጻጻፍና የንባብ ስያሜአቸውን ማቅረባችን የሚታወስ ነው፡፡ ዛሬ ደግሞ የሰውነት ክፍሎችን ማቅረባችንን እንቀጥላለን፡፡

የሰውነት ክፍሎች፣ ከአንገት በላይ የአካል ክፍሎች፣ /ክፍላተ አካላት ዘላዕለ ክሳድ/

የአንገት በላይ የአካል ክፍሎች ማለት ከእራስ ፀጉራችን ጀምሮ እስከ አንገታችን ድረስ ያሉትን የአካል ክፍሎች ያካተተ /የያዘ/ ክፍል ማለት ነው፡፡ እነዚህንም የአካል ክፍሎች ከዚህ በመቀጠል እንመለከታለን፡፡
ሰብእ – ሰው

– ሰብእ ዘተፈጥረ እምነ ሠለስቱ ባሕርየተ ነፍስ ምስለ አርባዕቱ ባሕርያተ ሥጋ ውእቱ
    ሰው የተፈጠረው ከሦስቱ ባሕርያተ ነፍስ እና ከአራቱ ባሕርያተ ሥጋ ነው፡፡

– ሠለስቱ ባሕርያተ ነፍስ ብሂል
    ሦስቱ ባሕርያተ ነፍስ ማለት

፩. ሕያዊት – ሕዋሳትን የምታንቀሳቅስ ሕይወት ያላት
፪. ለባዊት – ልብ የምታደርግ /የምታስብ/
፫. ነባቢት – የምትናገር

አርባዕቱ ባሕርያተ ሥጋ ብሂል
 አራቱ የሥጋ ባሕርያት ማለት 

  • ነፋስ –  የነፋስነት ባሕርይ           – አፍ – አፍ
  •   እሳት – የእሳትነት ባሕርይ          – ስን – ጥርስ
  • ማይ – የውኃነት ባሕርይ            – ልሳን – ምላስ
  •   መሬት – የመሬትነት ባሕርይ        – ቃል – ቃል
  •   ድማሕ /ናላ/ – መሀል ራስ /አናት/  – ዕዝን – ጆሮ
  • ናላ – አናት                          – መልታህ – ጉንጭ
  •  ስእርት – የራስ ፀጉር                – አንፍ – አፍንጫ  
  • ጽፍሮ – ሹርባ                       – ከንፈር – ከንፈር
  • ድንጉዝ – ጥቅል ሥራ               – ሕልቅ – አገጭ
  • ድምድማ – የተበጠረ ጎፈሬ          – ጽሕም – ጢም
  • ሲበት – ሽበት                       – ክሳድ – አንገት
  •  ገጽ – ፊት                           – ምጉንጳ – የዐይን ሽፋን
  • ፍጽም – ግንባር                     – ዓይን – ዐይን
  • ከዋላ – ኋላ                                     የድምጽ ክፍላት
  • ቅርንብ – ቅንድብ                   – ፋጻ – ፍጨት            
  • ዕዝን – ጆሮ                         – ጒሕና – ጎርናና /ወፍራም/ ድምጽ   
  •  መልታህ – ጉንጭ                  – ቃና – የዜማ ድምጽ,  እስትንፋስ – ትንፋሽ 

ክርስትና “አክራሪነት”ን የሚያበቅል ነገረ ሃይማኖታዊ መሠረት የለውም

ነሐሴ 21 ቀን 2005 ዓ.ም.
 
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሀገራችን የሃይማኖት “አክራሪነት” ስጋት እንዳለ በተለያዩ ወገኖች የሚነሣ ሐሳብ አለ፡፡ የ “ሃይማኖት አክራሪነት” በሀገራችን የለም የሚል እምነት አይኖርም፡፡ “አክራሪነት” የሚተረጎመውም የራስን የሃይማኖት የበላይነት ለማስፈን ሲባል ሌላው የሃይማኖት ሐሳቡን እንዳይ ገልጥ፣ ተግባራዊ የአምልኮ ሥርዓቱን እንዳይፈጽም ማድረግ፣ በኃይል ወይም በዐመፅ ቦታ ማሳጣት ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ አንድ ቤተ እምነት ራሱ ከሚከተለው እምነት ውጪ ያሉ በቁጥር ትንሽ ወይም ብዙ ተከታይ ያሏቸው እምነቶች በአንድ ሀገር ወይም ቦታ መኖር የለባቸውም ብሎ ማመን ወይም ማድረግ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ይህ ደግሞ የሰዎችን የፈቃድ ነጻነት፣ ምርጫ አለማክበር፤ አለመጠበቅ ነው፡፡

ከላይ የተጠቀሰው አስተሳሰብ ደግሞ በምንም መስፈርት ቢመዘን ክርስትና ሊሸከመው የሚችለው አይደለም፡፡ የሚጋጨውም ከክርስትና መሠረታዊ ባሕርይና አካሔድ ጋር ነው፡፡ ክርስትና ወደ ሰዎች የመጣው በራሱ በሥግው አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ሥራና ቃል ነው፡፡ ጌታችን ወደ ሰዎች ቀርቦ ወደ እርሱ እንዲመጡ የሳባቸው የፈቃድ ነጻነታቸውን ጠብቆ ነው፡፡ በደዌ ነፍስ የተያዙትን በትምህርቱ፣ በደዌ ሥጋ የተያዙትን በተኣምራቱ ሲፈውስ ሁሉንም “ልትድን ትወዳለህን” እያለ ፈቃዱን ጠይቆ የፈጸመው ነበር፡፡ ልባቸው ወደ እርሱ ያዘነበሉትን “ተከተሉኝ” ብሎ ወደ መንግሥቱ እየጋበዘ ከእርሱ ኅብረት ደምሯቸዋል፡፡ “ሸክማችሁ የከበደ ወደ እኔ ኑ፤ እኔም ዐሳርፋችኋለሁ” ብሏቸዋል፡፡

ጌታችን ያለፈቃዳቸው ከጉባኤው የደመራቸው ወገኖች አልነበሩም፡፡ ተሰብስበውም ከነበሩት የሚያስተምረው ኃይለ ቃል ከምስጢሩ ታላቅነት የተነሣ የጸነናቸው ታዳሚዎች እንኳን ጥለውት በሔዱ ጊዜ አልተቃወመም፡፡ በእግሩ ስር የቀሩ ሐዋርያቱንም “እናንተስ ልትሔዱ ትወዳላችሁን” እያለ ደቀመዛሙርቱን እንኳን ፈቃዳቸውን ያረጋግጥ ነበር እንጂ፤ ከዋልኩበት ውላችሁ፣ ካደርኩበት አድራችሁ፤ አበርክቼ አብልቼ፣ በፍቅሬ ረትቼ፤ በተአምራቴ ፈውሼ፣ ተኣምራት የምትሠሩበትን ኃይል አልብሼ ካቆየኋችሁ በኋላ ስለምን ትተውኛላችሁ ብሎ አምላካዊ ሥልጣኑን ተጠቅሞ ሊጫናቸው አላሰበም፡፡ በመሆኑም ክርስትና “ከአንተ ወደ ማን እንሔዳለን” ያሉ ቅዱሳን ሐዋርያትና በሐዋርያት ትምህርት የጸኑ፣ እስከ ዓለም ፍጻሜ የሚነሡ ምእመናን በፈቃዳቸው የሚኖሩበት ሃይማኖት ነው፡፡   

ጌታችን እንድንቃወም ያስተማረን ሌሎችን በኃይል ወደ እርሱ መሳብን ብቻ ሳይሆን ሊያስገድዱን የሚመጡ፣ መልካሙን እንዳንፈጽም የሚከለክሉንንም ቢሆን በኃይል ለመቋቋም መሞከርንም ነው፡፡ ጌታችን ለጴጥሮስ “ሰይፍን የሚያነሡ በሰይፍ ይጠፋሉ፤ ሰይፍህን ወደ ሰገባው መልስ” ያለው ለዚህ ነበር፡፡ ለዚህም ነው ክርስትና በባሕርዩ “አክራሪነት”ን የሚያስተ ናግድበት መስክ የለውም፤ በጽኑም ይቃወመዋል፡፡

ክርስትና ሰዎች የእምነት ሐሳባቸውን እንዳይገልጹ አይገ ድብም፡፡ ሌሎች በእምነቱ ላይ ያላቸውን ጥያቄ እንዳያቀርቡም አይከለክልም፡፡ ስለያዘው እውነት በራሱ የሚተማመን ሃይማኖት ነው፡፡ ስለሆነም እርሱም ይሔንኑ መብት በጽኑ ይፈልገዋል፡፡ ለሚጠይቁት ሁሉ መልስ ለመስጠት የተዘጋጀ፣ የራሱን የድኅነት መንገድ ለመመስከር የተሰማራ ሃይማኖት ነው፡፡ የክርስቶስን መንግሥቱንና ጽድቁን ለሚሹ ሁሉ “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ” እያለ ይጮኻል፡፡ ስለዚህ ክርስትና የ “አክራሪነት” ሐሳብ ከመሠረቱ ሊበቅልበት የማይችል ሃይማኖት ነው፡፡

በተግባርም ቢሆን ከቤተልሔም ዋሻ አንሥቶ እስከ ምድር ጥግ እንዲስፋፋ ያስቻለው በረድኤተ እግዚአብሔር ተደግፎ፣ በፍቅር ስቦ፣ በመግደል ሳይሆን በመሞት የብዙዎችን ነፍስ ለመታደግ የሚኖር ሃይማኖት በመሆኑ ነው፡፡ ስለዚህ የቃለ ሃይማኖቱን ኃይል የተአምራቱን ብዛት የአማኞቹን ጽናት አይተው የራሳቸውን እምነትና ፍልስፍና ለመጫን የሞከሩበትን አምልኮ ባዕዳንን ይከተሉ ከነበሩ ወገኖች ጀምሮ ሃይማኖትን የዕድገት፣ የነጻነት፣ የፍትሕ፣ የእኩልነት ወዘተ ጸር አድርገው እስከሚያስቡ የማርክሲዝም ሌኒንዝም ተከታዮች ድረስ የነበሩ “አክራሪዎች” ክርስትናን ሊያጠፉት ሲሞክሩ ታይቷል፡፡ ነገር ግን ሰይፋቸውን በትዕግስት ተቋቁሞ፣ እነርሱ እያለፉ እርሱ ሳያልፍ ዘላለማዊ ሆኖ እዚህ የደረሰ ሃይማኖት ሆኗል፡፡

ክርስትና በ“አክራሪነት” ሲመላለስ አልኖረም፡፡ በክር ስትና ስም የሚፈጸሙ ወይም በታሪክ ወስጥ የተፈጸሙ አሁን “አክራሪነት” ያልነው ጠባይ የተንጸባረቀባቸው አጋጣሚዎች ቢኖሩ እንኳን በክርስትና ስም ልንቀበለው የምንችለው አይሆንም፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም “ቢቻላችሁስ ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ” የሚል የፍቅር ቃል ሰጥተውናል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንም ሐዋርያዊ ውርስ ያላት ጥንታዊ ቤተክርስቲያን ስትሆን እነዚህ ከላይ የተሰጡ፣ ጌታችን መድኅኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረውን ትምህርትና ቅዱሳን ሐዋርያት ያስተላለፉትን መልእክት ታከብራለች፤ ትጠብቃለች፤ ነገረ ሃይማኖታዊ መሠረቷም ይኸው ነው፡፡

ስለዚህ ቤተክርስቲያን የእኔ ናቸው በምትላቸው ሕጋዊ መዋቅሮቿ፣ በመዋቅሮቿም ላይ የሚያገለግሉ አገልጋይ ካህናትና ምእመናን ሰንበት ትምሀርት ቤቶችና ማኅበራት ሁሉ ከላይ ከተጠቀሰው ክርስቲያናዊ መንገድ የወጣ በ”አክራሪነት” የሚታሰብባቸውን ተግባራት ሊፈጽሙ አይችሉም፤ ካደረጉም ቤተ ክርስቲያኒቱ ባላት ቀኖናዊ ሕግ መሠረት ይዳኛሉ፡፡ ይታረማሉ፤ ካልሆነም ይለያሉ፡፡

ቤተክርስቲያን ያላት ነገረ ሃይማኖታዊ ሐሳብ ይህ መሆኑን ከተስማማን፣ በዚህ መሠረታዊ አስተምህሮዋ ላይ ቅሬታ የሌለን ከሆነ፣ መልካምነቱን የምንረዳ ከሆነ፣ በዚህ ላይ ያልበቀለ፣ ያላፈራ፣ መልካም ያልሆነ የቤተክርስቲያን እንቅስቃሴ ካለ መመርመር ይገባል፡፡ በዚህ ጊዜ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “መልካም ዛፍ ሁሉ መልካም ፍሬን ያፈራልና፤ ክፉ ዛፍም ክፉ ፍሬን ያፈራል፤ መልካም ዛፍ ክፉ ፍሬን ማፍራት፣ ክፉ ዛፍም መልካም ፍሬን ማፍራት አይችልም፤ መልካም ፍሬን የማያፈራ ዛፍ ሁሉ ይቆረጣል፤ ወደ እሳትም ይጣላል እግዲህ ከፍሬያቸው ታውቋቸዋላችሁ” /ማቴ 7፥17/ ያለው ቃሉን እናስባለን፡፡ 

 
ማኅበረ ቅዱሳንም ከዚህ የወጣ አካሒድ ሊኖረው አይችልም፡፡ በቤተክርስቲያኒቱ መዋቅር ውስጥ ያለ ሓላፊነት የሚሰማው የአገልግሎት ማኅበር ነውና፡፡ “አክራሪነት”ን በመቃወምና የሃይማኖቶችን መከባበር ተገቢነት አስመልክቶ በተደጋጋሚ በገለጻቸው አቋሞቹ አስታውቋል፡፡ ለዚህም በሐመር መጽሔት በግንቦት ወር 2001 ዕትም፣ ስምዐ ጽድቅ በርእሰ አንቀጹ በጥቅ ምትና በኅዳር 1999 ዕትም፣ መጽሔተ ተልእኮ ዘማኅበረ ቅዱሳን በምንለው የማኅበሩ የሕዝብ ግንኙነት መጽሔት በነሐሴ 2004 ዓ.ም ዕትም በዚሁ ጉዳይ ያለውን አቋም ገልጿል፡፡  

ይሁን እንጂ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ “አክራሪነት” እንዳለና አልፎ አልፎም “ማኅበረ ቅዱሳን” ብለው በስም ጠቅሰው ለመፈረጅ የሞከሩ በአንዳንድ አካባቢ ያሉ መንግሥት ያዘጋጀውን የውይይት መድረክ የተጠቀሙ አስፈጻሚዎች ነበሩ፡፡ እነዚህ አልፎ አልፎ መንግሥት “አክራሪነት”ን ለመከላለከል ለሚወስዳቸው እርምጃዎች አጋዥ የሚሆን ውይይት በየደረጃው በሚያደርግበት አጋጣሚ የማኅበረ ቅዱሳንን ስም በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ ይታያል ላሉት “አክራሪነት” ማሳያ አድርገው ማቅረባቸው ለማኅበሩ አባላት ደስ የሚያሰኝ አልነበረም፡፡

“አክራሪነት” ከላይ በጠቀስነው እሳቤ መሠረት የሚታይ ከሆነ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ላሳዩት የ‹‹አክራሪነት›› ጠባይ ግልጽና ተጨባጭ ማስረጃ ማቅረብ ያሻል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ከዚህ ቀደምም ከማንም በፊት በሀገራችን የአክራሪነት ዝንባሌዎች እንዳሉ በማመልከት በኩል ግንባር ቀደም ሚና ተጫውቷል፡፡ “አክራሪዎች” በተለያዩ አካባቢዎች አብያተክርስቲያናትን ሲያቃጥሉ ክርስቲያኖችን ሲያርዱ አካሔዱ መልካም አለመሆኑን በመጠቆም እርምጃ መውሰድ እንደሚገባ በማሳሰብ ሀገራዊ ሓላፊነቱን ለመወጣት ሞክሯል፡፡ የሃይማኖቶች መከባበር በመላው ሀገሪቱ እንዲሰፍን ያለውን ቁርጥ አቋምም አንጸባርቋል፡፡

በእርግጥ ማኅበረ ቅዱሳን ቤተክርስቲያናችን ጠንካራ የአስተዳደር፣ የአሠራር፣ የአገልግሎት አካሔድ እንዲኖራት አቋም ይዞ የሚያገለግል ማኅበር ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ካህናትና ምእመናን ሁሉ የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ቃል አክብረው፤ የሐዋርያትን የሊቃውንት አባቶችን የሃይማኖት ትምህርት፣ ሥርዓት፣ ታሪክና ትውፊት አውቀው እንደ ሃይማኖቱ ሕግና ሥርዓት እንዲመላለሱ ያተጋል፡፡ የተዘጉ አብያተ ክርስቲ ያናት እንዲከፈቱ፣ ሊቃውንቱ በረሃብ በችግር ተፈተው ከአገልግሎት እንዳይቦዝኑ ለማድረግ ይተጋል፡፡ የሌላ ቤተእምነት ተከታዮች በቤተክርስቲያን ትምህርት ላይ ለሚያነሧቸው ጥያቄዎች መልስ በመስጠት የዕቅበተ እምነት ሥራ ይሠራል፡፡

 

በኮሌጅና በዩኒቨርሲቲ ትምህርታቸውን እየተከታተሉ ያሉ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ካደጉበት መንደር /ቀዬ/ ርቀው ወደ ተለያዩ ትምህርት ተቋማት ሲመጡ በአቅራቢያ በሚገኙ አጥቢያዎች ሰብስቦ በሃይማኖታቸው ተጠብቀው እንዲኖሩ፣ በመልካም ሥነምግባር ታንጸው ሀገራቸውንና ቤተክርስቲ ያናቸውን በታማኝነት እንዲያገለግሉ፣ ከሱስና ከዝሙት ተጠብቀው ከደዌ ሥጋ ደዌ ነፍስ እንዲርቁ ያደርጋል፡፡ በጠረፋማ አካባቢዎች ስብከተ ወንጌልን ያስፋፋል፡፡ በጤናና ትምህርት ጉዳዮችም በማኅበራዊ አገልግሎት ተሳትፎ እንዲኖረው እየጣረ ነው፡፡ እነዚህ ተግባራቱ ሁሉ ከቤተክርስቲያኒቱ የአገልግሎት መንፈስ የተቀዱ ናቸው፡፡ ለየትኛውም ወገን ቢሆን የሚጠቅሙ እንጂ ስጋት የሚሆኑ ተግባራት አይደሉም፡፡ በሃያ ዓመት የአገልግሎት ቆይታውም ያስመዘገባቸው ውጤቶች በስጋት ሳይሆን በአስፈላጊነት ሊያስፈርጀው የሚችል ነው፡፡

ስለዚህ የትኛውም ወገን ቢሆን እውነታውን ለመረዳት ጥረት ማድረግ ይገባዋል፡፡ ቸግሮች አሉ ቢባሉ እንኳን ተገቢነት ከሌላቸው ዘመቻዎች ቆጠብ ብሎ ከቤተክርስቲያኒቷ አባቶችና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር አግባብነት ያላቸው ውይይ ቶችን ማድረግ በቂ ይሆናል፡፡ ማኅበሩ የቤተክርስቲያኒቱ ሉዓላዊ ሥልጣን ባለቤት የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ እንዲሠራ ከሰጠው ተግባራት ውስጥ ወደ ‹‹አክራሪነት›› አምባ ያስገባውን ወሰን አለፈ ያስባሉትን ነጥቦች ነቅሶ ማሳየት፣ እንዲህ የሚያስብሉ የተፈጸሙ ተግባራትንና ተግባራቱን ማኅበሩ ሓላፊነት ወስዶ የፈጸመው ተግባር መሆኑን የሚያሳዩ ማስረጃዎችን ማቅረብ አግባብ ይሆናል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ሁልጊዜም ቢሆን የሃይማኖት አባቶች የሚያዙትን እንጂ ከዚያ ተላልፎ በራሱ ፈቃድ የሚፈጽመው አንዳችም ተግባር አለመኖሩን መረዳት ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

  • ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት 21ኛ ዓመት ቁጥር 4 ነሐሴ 2005 ዓ.ም.

 

debre tabor

የምሥጢር ቀን

ነሐሴ 13 ቀን 2005 ዓ.ም.

ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መላክ  
በምዕ/ጐጃም ሀገረ ስብከት የ፬ቱ ጉባኤያት መምህር

debre taborየአምላክ ሰው መሆን አንዱ ምክንያት ምሥጢረ መለኮት ለተሰወረበት ዓለም ምሥጢረ መለኮትን መግለጥ ነው፡፡ ክፉውንና ደጉን ለይቶ ከሚያስታውቀው ዛፍ የተነሳ ከ8ኛ መዐርግ  ላይ ሆኖ በመፈጠሩ የተሰጠውን ከፍተኛ የዕውቀት ፀጋ ክፉ ዕውቀት ስለተጨመረበት ለነፍሱ ምሥጢረ መለኮትን ማወቅ የሰው ልጅ ተስኖት ነበር ፡፡ ጌታችን ወደዚህ ዓለም ሲመጣ  ዓለም ምንም ምሥጢር የላትም ነበር፡፡ ምሥጢራት ሁሉ በልበ መለኮት ተሰውረው ይኖሩ ነበር እንጂ፡፡ በሌላ አነጋገር የተፀነሰ ምሥጢር እንጂ የተወለደ ምሥጢር አልነበረም ማለት ነው፡፡ ለዚህ አይደል መድኀኒታችን እየሱስ ክርስቶስ  ለደቀ መዛሙርቱ ከሕዝብ ለይቶ ምሥጢራትን ይነግራቸዉ የነበረው ማቴ.13 ፥11፡፡ በቀዳማዊው ሰው በአዳም በኩል ለሰው ልጀች ሁሉ የተሰጠው የመንግሥቱ ምሥጢር ዳግም በሁለተኛው ሰው በክርስቶስ በኩል ካልተገለጠ በሌላ በምን ይገለጣል!!  ለዚህም በአብ ልብነት ተሰውሮ ይኖር የነበረው ብቸኛ ምሥጢር እርሱ ሆኖ  ሳለ ከልደቱ ጀምሮ የመንግሥቱን ምሥጢር በብዙ መንገድ ገለጠ፡፡

ሐዋርያው ጳውሎስ እንደተናገረው ለቀደሙት ሰዎች በብዙ መንገድ በብዙ ኅበረ አምሳል ምሥጢራትን ይናገር  የነበረ እግዚአብሔር አወጣጡ ከጥንት በሆነውና  ተቀዳሚ ተከታይ በሌለው በአንድ ልጁ  በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ተናገረን ዕብ 1፥1-2 ፡፡ ማንም ያየው የሌለ እግዚአብሔርነቱን ወደ ዓለም መጥቶ ተረከው፡፡ በልደቱ ቀን ከገለፀልን የተነሳ “ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት” ብለን ዘመርን፡ እግዚአብሔር ገለጠልን፡፡ “ይህንን ምሥጢር እናይ ዘንድ ኑ! እስከ ቤተልሔም እንሒድ” ሉቃ.2፡15 ብለው ሲናገሩ ከእረኞች አፍ መስማታችንስ ልደቱ ሊያዩት የሚገባ ምሥጢር መሆኑን የሚያሳይ አይደል፡፡ የሶርያው ሊቅ ቅዱስ ኤፍሬም ይህን ሲያፀናልን “ንዑ ርዕዩ ዘንተ መንክረ ይህን ድንቅ ምሥጢር ታዩ ዘንድ ኑ!” በማለት ምሥጢርነቱን በማወጅ ሕዝቡን ይጠራል፡፡

በሰው ሊገለጥ ያለው ምሥጢር ይህ ብቻ  አልነበረም፡፡ በቤተ ኢያኢሮስ በአደረገው የማዳን ሥራ ምሥጢረ ድኅነትን፤ በቤተ አልዓዛር በአደረገው ሞትን የማሸነፍ ሥራ ምሥጢረ-ትንሣኤ ሙታንን፤ ወዙ እንደ ደም ወይቦ እስኪወርድ ድረስ በጌቴ ሴማኒ ምሥጢረ ጸሎትን ካሳየ በኋላ ደገኛውን ምስሥጢር በዕለተ አርብ መጋረጃው ተቀዶ የሰው ልጅ ባሕረ እሳትን ተራምዶ እስክናይ ድረስ ታላቅ ምሥጢርን በደብረ ታቦር ገለጠልን፡፡

ጌታ ሊገልጠው የፈለገውን ማንኛውንም ምሥጢር ሦስት ነገሮችን መምረጥ የሁልጊዜ ተግባሩ ነው፡፡ ምሥጢሩን የሚገልጥበት ቦታ፣ ጊዜ እና ሰው ናቸው፡፡ በደብረ ዘይት የገለጠውን በደብረ ታቦር፣ በጌቴ ሴማኒ የገለጠውን በዮርዳኖስ፤ ለነቢያት የገለጠውን ለሐዋርያት አይገልጠውም፡፡  በተለይ በሐዋርያት ልቦና ቆልፎ ያኖረውን ከሁሉም በላይ ደግሞ በእመቤታችን ልቦና የሰወረውን ምሥጢሩን ማን ያውቀዋል?? አበው እንደነገሩን በልበ ሐዋርያት ተሰውሮ የቀረውን የወንጌል ምሥጢር እስከ ዓለም ፍፃሚ  የሚያውቀው የለም ብለውናል፡፡  ምክንያቱም የሐዋርያትን ክብር ከላገኙ ሐዋርያት ያወቁትን ማወቅ ስለማይቻል ነው፡፡ ከሐዋርያት በኋላ ተነስቶ  ወደ ሐዋርያት መዐርግ  መድረስ ከተቻለው ከቅዱስ ጳዉሎስ በቀር የተሳካለት ማንም የለም፡፡ ዛሬ ክብር ይግባውና መድኃኒዓለም ክርስቶሰ በደቀ መዛሙርቱ ልብ ሊያስቀምጠው የፈለገው አንድ ታላቅ ምሥጢር አለው በጊዜው ጊዜ የሚነገር ከትንሣኤ በኃላ በሚዘከር እንጂ በማንኛውም  ጊዜ የማይነገር አዲስ ምሥጢር ነው፡፡ ታዲያ ለዚህ ታላቅ ምሥጢር መገለጫ ትሆን ዘንድ የተመረጠችው ደግሞ ደብረ ታቦር ተራራ ናት ፡፡

ደብረ ታቦር ለምን ተመረጠ?
1.    ትንቢቱ፤ ምሳሌው ሊፈፀም፡-  
በቀደመው ዘመን ነቢያት ትንቢት ከተናገሩላቸዉ ቅዱሳት መካናት አንዱ ደብረ ታቦር ነው፡፡ ነቢዩ ዳዊት በመዝሙሩ “ታቦር ወአርሞንኤም በስመ ዚአከ ይትፌስሑ ታቦርና አርሞንኤም በአንተ ስም ደስ ይላቸዋል” መዝ፡ 188÷12 በማለት ከደብረ ታቦር እስከ አርሞንኤም በደረሰው የመለኮት ብርሃን የተፈጠረውን ደስታ ሲገልጥ እንሰማዋለን፡፡ ምንድን ነው ይህ ደስታ? ሊባል ይችላል፡፡ ነብዩ ከአንድ ሺህ ዓመት በኋላ ስለሚደረገው ተራሮችንና ኮረብቶችን ሳይቀር ያስፈነደቀ ደስታ በእውነት ይህን ተናገረ፡፡ ምናልባት “በአንተ ስም ደስ ይላቸዋል” ብሎ ለሰው በሚናገር መልኩ ግዑዛን ለሆኑ ተራሮች መናገሩ ሊያስገርም ይችል ይሆናል፡፡  የሰው የደስታው መገለጫ የገፁ ብሩህነትም አይደል? እነዚህም ተራሮች በዚህ ዕለት በተገለጠው የመለኮታዊ ክብሩ ነፀብራቅ ጨለማ ተወግዶላቸዉ የፀሐይን ብርሃን በሚበዘብዘው አምላካዊ ብርሃን፣ ብርሃን ሆነው የዋሉበት ቀን ነውና ነቢዩ ለሰው በሚናገርበት ግስ ይናገርላቸዋል፡፡ ሌላም ምሥጢር አለው ይላሉ ሊቃውንቱ፡፡

 

በተራሮች ስም የተጠሩት ልዑላኑ የጌታ ደቀ መዛሙርት ነቢያትና ሐዋርያት እና ልዑላኑ አገልጋዩችህ በጌታ ስም ደስ ይላቸዋል ማለት ነው ብለውታል፡፡ ምሳሌ በአባቶቻችን ዘመን በዚህ ቅዱስ ተራራ ጽኑ ሰልፍ እንደተደረገ የመሳፍንቱ ታሪክ በተፃፍበት መጽሐፍ እናነባለን መሳ.4 ፥1፡፡ በእሥራኤል ላይ ገዥ ሆኖ የተነሣው በክፉ አገዛዙም ምክንያት እሥራኤልን ያስለቀሰው አሕዛባዊው የሠራዊት አለቃ ድል የተነሳው በዚሁ ሥፍራ ነበር፡፡ ደብረ ታቦር 9 የብረት ሠረገሎች የነበሩትን ባለ ሠራዊት ሰው ሲሳራን ድል ለማድረግ ምቹ ቦታ ነበር፡፡ ያውም በጥቂት ኃይል በሴቲቱ ነብይት በዲቦራ በሚመራ የጦር ሰራዊት ፡፡ ይህ በእውነት በኋለኛው ዘመን ለሚደረገው የድል ዘመን ጥላ አባቶቻችንን በብረት በትር ቀጥቅጦ የገዛውን ባለ ብዙ ሠራዊት ዲያብሎስን ከሴቲቱ ነብይት የተወለደው የይሁዳ አንበሳ ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ቅዱስ ሥፍራ ድል እንደሚያደርግላቸዉ እሥራኤል ዘነፍስም ነፃ እንደሚያወጣቸው የሚያሳይ ምሥጢር ነበረው፡፡ ሲሳራን፤ ባራቅ እና ዲቦራ ድል ያደርጉታል ተብሎ ታስቦ ነበርን ? ይልቁንም ሲገዛን ሊኖር አስቦ አልነበረምን? የድንግል ልጅ መድኀኒታችን ክርስቶስ ግን የሲዖልን በሮች ሰብሮ ጠላታችንን በጽኑ ሥልጣን አስሮ እኛን ነፃ አወጣ፡፡ ታዲያ ምሳሌው አማናዊ የሚሆንበትን ዘመን መድረሱን ሊያበስራቸዉ ወደ ደብረ ታቦር ወጣ፡፡ 

2.     ደብረታቦር ሁሉን የሚያሳይ ቦታ ስለነበር፡-
ደብረ ታቦር ሆኖ ዓለምን ቁልቁል መመልከት ይቻላል፡፡ የተራራው ጫፍ ላይ ሆኖ  ሲመለከቱ ሁሉም ግልጥ ነው ፡፡ ለዚህ ነው ቅዱስ ዼጥሮስ  በዚህ ቦታ መኖርን የተመኘው “ሰናይ ለነ ሀልወ ዝየ- በዚህ መኖር መልካም ነው” (ማቴ.17÷5) ሲል ነበር ፍላጐቱን የገለጠው፡፡  ከሁሉ በላይ ሆኖ ሁሉን እያዩ ሚኖሩበት ከፍ ያለ ቦታ ነውና፡፡ እግዚአብሔር ግን ይህንን በምሥጢር አደረገ፡፡ ከዘመናት አስቀድሞ የተሰወረውን ምሥጢር ለሁሉ ግልጽ ሊያደርግ አስቦ ሁሉን ወደሚያሳየው ቦታ ወሰዳቸዉ፡፡ በክርስቶስ ሰው መሆን ያልታየ ምሥጢር ያልተገለፀ ድብቅ ነገር የለምና፡፡  ለዚህ አፈ- በረከት ተብሎ የሚጠራው ቅዱስ ኤፍሬም በረቡዕ ውዳሴ ማርያም ላይ “የማይታወቅ ተገለጠ የማይታይ ታየ” ሲል የተናገረው፡፡ አሁን  የማይታየውን እግዚአብሔርን የምናይባት ድብቁን የእግዚአብሔርን ነገር በእምነት የምናስተውልባት አማናዊቷ የታቦር ተራራ ቤተ ክርስቲያን፡፡ በእርሷ ውስጥ የሚኖሩ ሁሉ ዓለምን ቁልቁል እየተመለከቱ ጣዕሟን ሲንቁባት ይኖራሉ፡፡ ከሷ ተለይቶ ከላይ ሆነው ከተራራው ጫፍ ስለሚመለከቷት ቤታቸዉን በተራራው ለማድረግ ይመኛሉ፡፡ ሁልጊዜም “እግዚአብሔርን አንዲት ልመና ለመንሁት እሷንም እሻለሁ በህይወቴ ዘመን ሁሉ በእግዚአብሔር ቤት እኖር ዘንድ” መዝ ፡ 26፡4  እያሉ ይዘምራሉ፡፡ ምክንያቱም በዚህ ዓለም ውስጥ ሁኖ ታቦርን ማየት አይቻልም፡፡ በታቦር ላይ ሆኖ የዓለምን ምሥጢር ማወቅ  ይቻላል፡፡ 

3.    በተራራ የተነጠቅነውን ፀጋ በተራራ ለመመለስ
አዳም እንደ አጥቢያ ኮከብ የሚያበራ ግርማው የሚያስፈራ ብርሃናዊ ፍጡር እንደ ነበር፤ ስነ ተፈጥሮውን የሚናገሩ መጽሐፍት ምስክሮቻችን ናቸዉ፡፡ ይህንን ብርሃናዊ የፀጋ ልብሱን ተጐናጥፎ የተቀመጠው በእግዚአብሔር ተራራ በገነት ነበር፡፡ ከመጀመሪያው ጀምሮ የጠላት ዐይን አርፎበት ኖሮ ከጥቂት አመታት በኃላ ይህን ብርሃናዊ ልብሱን ለብሶ እንደ ማለዳ ኮከብ ሲያበራ መኖር አልተቻለውም፡፡ እናም በዚያው በእግዚአብሔር ቅዱስ ተራራ ላይ ሳለ ይህን ፀጋውን ባለማወቅ ተገፈፈ፡፡ የክርስቶስ ወደዚህ ዓለም መምጣት የተቀማነውን ለማስመለስ አይደል፡፡ ስለዚህም በዚህ ቅዱስ ተራራ ላይ ለደቀ መዛሙርቱ በገለጠው ብርሃን ላይ ተስፋን አስጨበጠን፡፡ ቅዱስ ወንጌል እንደተናገረው በዚህ ዕለት ሐዋርያት ነቢያት በተገኙበት በዚህ ሥፍራ የክርስቶስ ሦስት ክንድ ከስንዝር አካሉ ብሩህ ሆነ፤ ልብሱም ከበረዶ ይልቅ ነጭ ሆነ፡፡

 

የሰው ልጅ ከቅዱስ ተራራ ከገነት ከወጣበት ጊዜ ጀምሮ እንዲህ ሆኖ  አያውቅም፡፡ ሰውነቱ በኀጢያት በልዞ በበደል መግነዝ ተገንዞ የሚያስቀይም መልክ ነበር እንጂ እንደዚህ የአማልእክት ልጆችን አይነት መልክ መች ነበረው? ዛሬ ግን  እንደዚያ አይደለም፡፡ የአዳም አካል መልኩ ተለውጧል፡፡ ከጥቁረቱ ነጥቷል፡፡ ወንጌላውያን ይህን ሲገልጡት “ወተወለጠ ራዕዩ በቅድሜሆሙ፣ መልኩ በፊታቸዉ ተለወጠ” ማቴ17፥2፤ማር 9፥2፡፡ ኢትድጵያዊ ቄርሎስ ተብሎ የሚጠራው የሀገራችን ሊቅ ቅዱስ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ይሄን ሲተረጉም ክርስቶስ በዚህ ዕለት የተገለጠው አዳም ከበደል በፊት በነበረው መልኩ እንደነበረ መጽሐፈ  ምስጢር በተሰኘው  ድርሳኑ ይናገራል፡፡ ያማ ባይሆን ኖሮ ደብረ ታቦር እንደምን ልፍረስ አልፍረስ አላለችም፡፡ ምክንያቱም ሊጦን በተሰኘው ምስጋናችን ውስጥ ስለእግዚአብሔር ስንናገር የምንለውን እናውቃለን፡ “ዘይገሥሶሙ ለአድባር ወይጠይሱ – ተራሮችን በእጁ ሲዳስሳቸው የሚጤሱት” ብለን አይደል የምናመሰግነው፡፡ 

ታቦር ታዲያ እንደምን አልተናወጠችም? ለሙሴ እንኳን በተገለጠበት በዚያ በመጀመሪያው ተራራ የተደረገው እንደዚህ አልነበረም፡፡ ሕዝቡ የሚደርሱበትን አጥንው  እስኪንቀጠቀጡ ድረስ  ከባድ የመብረቅና  የነጐድጓድ  ድምፅ  በተራራው ላይ  ነበር ዘጸ.19÷18፡፡ የዛሬው ግን ከዚያ  ልዩ ነው፡፡ ምንም እንኳን ከተገለጠው ክብር የተነሳ በዙሪያ የነበሩትን እንደ በድን ያደረገ የብርሃን ነፀብራቅ ቢኖርም ቅሉ ለቀደመው ሰው ለአዳም ከመርገም በፊት የነበረውን የፀጋ ግርማ ሞገስ የሚያሳይ ነው እንጂ ሌላ ምን ይሆናል? አብርሃም ዮርዳኖስን ተሻግሮ የተገናኘውን ሰው የመልከጸዴቅን ግርማ በአይኖቹ መመልከት አልችል ብሎ መልከጸዴቅ ቀርቦ እስኪያነሳው ድረስ በፊቱ እንደ በድን ሆኖ የወደቀ አይደለምን? ከእግዚአብሔር ይነጋገር የነበረው የሙሴን ፊት ማየት ተስኗቸዉ የእስራኤል ልጆች አልፈሩምን? ይህማ ምን ይገርማል በእውነቱ ይህ ሁሉ የሆነው በቅዱሱ የእግዚአብሔር ተራራ በገነት የተነፈግነው ልጀነታችንን የሚያስፈራና የሚያስደነግጥ ግርማ ሞገሳችንን እንደመለሰልን ለማጠየቅ ነው፡፡ በመጀመሪያው ሰው ያጣነው የልጅነት መልካችንን በሁለተኛው ሰው አገኘነው፡፡

ዛሬ እስከ ዓለም ፍፃሜ ድረስ በቤተ ክርስቲያን በኩል ይህ ዕድል ሲታደል ይኖራል፡፡ ወንዶቹ በ4ዐ ቀን ሴቶቹ በ8ዐ ቀን ወደ ቤተ ክርስቲያን መጥተው በማየገቦ ተጠምቀው ዳግመኛ ከብርሃን ተወልደው ሰይጣንን የሚያስደነግጥ መልክ ይዘው እንደሚመለሱ በፍትሕ መንፈሳዊ በ3ኛው አንቀጽ ተመዝግቧል፡፡

ያስተውሉ!! ደብረ ታቦር የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናት፡፡ በደብረ ታቦር ነቢያትና ሐዋርያት  መዐስባንና ደናግል፣ አረጋውያንና ወጣቶች እንደተገኙ ሁሉ ቤተ-ክርስቲያንም በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ የታነፀች ናት፡፡ ለመዐስባንና ለደናግል፣ ለአረጋውያንና ለወጣቶች የተዘጋጀች የእግዚአብሔር መገለጫ ተራራ ነቸ፡፡ ከነቢያት 2ቱ ከሐዋሪያት 3ቱ መገኘታቸዉ ዛሬ በቤተ መቅደስ የሚያገለግሉት አምስት ልዑካን ምሳሌ ነው፡፡ እነዚያ ክርስቶስን እንደ  ታቦት በመሀል አድርገው ነበር የተገኙት፡፡ በቤተክርስቲያንም በቃል ኪዳኑ ታቦት ዙሪያ የክብሩን ዙፋን ከበው የሚቆሙት አገልጋዮች  በነዚያኞቹ አምሳል  የቆሙ ናቸው፡፡

egy fir

በግብፅ አብያተ ክርስቲያናትና ክርስቲያኖች የጥቃት ሰለባ እየሆኑ ነው

ነሐሴ 11 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

egy firየፕሬዚዳንት ሙሐመድ ሙርሲ ደጋፊዎች የሆኑት የሙስሊም ወንድማማቾች በግብፅ ኮፕት ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንና ክርስቲያኖች ላይ ከፍተኛ ጥቃት እየፈጸሙ እንደሚገኙ ዓለም አቀፍ የመረጃ ምንጮች በመግለጽ ላይ ናቸው፡፡ በተለይም በዲልጋ፤ ሚና፤ እና ሶሃግ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት የጥቃቱ ሰለባ እየሆኑ ነው፡፡ የሚና ቅድስት ማርያምና የአብርሃም አብያተ ክርስቲያናት የሙስሊም ወንድማማቾችና ደጋፊዎች በእሳት አያይዘዋቸዋል፡፡ ተቀጣጣይ ፈንጂዎችንም ሶሃግ በሚገኘው ማር ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ላይ ወርውረዋል፡፡

ከካይሮ የሚወጡ አዳዲስ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት በአንዳንድ አብያተ ክርስቲያናት ላይ የአልቃይዳ መለያ የሆነው ጥቁር ባንዲራ እየተሰቀለባቸው ሲሆን በተለይም የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ይገኝበታል፡፡

በላይኛው ግብፅም በርካታ አብያተ ክርስቲያናት እየተቃጠሉና ጥቃት እየደረሰባቸው ሲሆን ክርስቲያኖችም መገደላቸውን ከግብፅ የሚወጡ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ የኮፕት ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታዎድሮስ ከመንበረ ፓትርያርክ ቅዱስ ማርቆስ ካቴድራል ለመውጣት መገደዳቸውንም እነዚሁ ምንጮች ይገልጻሉ፡፡
አልጀዚራ እንደዘገበው ሊቢያዊው ታማር ረሻድ የተባለው ተቃዋሚ “ለፓትርያርክ ታዎድሮስ መልካም ዜና ልነግራቸው እፈልጋለሁ፡፡ በግብፅ ምድር ክርስቲያኖችና አብያተ ክርስቲያናት የማይኖሩበት ጊዜው ደርሷል” በማለት ለቴሌቪዥን ጣቢያው ሲናገር ተደምጧል፡፡

በላይኛው ግብፅ ከሚገኙት ሚና፤ አስዩትና ሶሃግ በተጨማሪ የክርስቲያኖች መኖሪያና የሥራ ቦታዎች በእሳት ተያይዘዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ሕይወታቸው አደጋ ላይ ወድቋል፡፡ አብያተ ክርስቲያናቱም አገልግሎታቸውን ማቋረጣቸውን ዓለም አቀፍ የዜና ምንጮች እየዘገቡ ይገኛሉ፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዝርወት ክፍል ሁለት

ሐምሌ 3 ቀን 2005 ዓ.ም

በዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ

ባለፈው ዕትማችን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ በዝርወት /ከኢትዮጵያ ውጪ/ ያደረገችውን ረዥም ሐዋርያዊ ጉዞ የሚዳስስ ጽሑፍ ማውጣታችን ይታወሳል፡፡ ቀጣዩን ደግሞ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡

2. አፍሪካ
የኢ.ኦ.ተ.ቤ. የጥቁሩን ሕዝብ መወከል የሚያስችላት ታሪካዊ አጋጣሚ ቢኖራትም ከዓለም ቀድማ በተመሠረተችበት አህጉር ለሚገኘው ሕዝቧ የሰጠችው አገልግሎት ሰፊ የሚባል አይደለም፡፡ እሷ አገልግሎት ባለመስጠቷ ጥቁሩ ሕዝብ ባሕሉና ልማዱ በፈጠረው ሀገረ ሰብአዊ እምነት ተይዞ ከአሚነ እግዚአብሔር ርቆ ለረጅም ዘመናት እንዲቆይ ሆኗል፡፡ አፍሪካውያን ከብዙ ሺሕ ዓመታት በኋላ ከኢትዮጵያ በእጅጉ ዘግይተው ወንጌልን የተቀበሉ አውሮ¬ውያን ያስተማሯቸውን ተቀብለዋል፡፡ ይልቁንም ቤተ ክርስቲያናችን ወደ ሕዝቡ መሔዷ ቀርቶ ራሱ ሕዝቡ እሷን ፈልጎ እንዲመጣ ኾኗል፡፡ በእርግጥ ቤተ ክርስቲያናችን ቀደም ባሉት ጊዜያት እስከ ሱዳንና ሱማልያ ተስፋ ፍታ እስልምና እስከሚቀማት ድረስ በርካታ አፍሪካውያንን በሃይማኖት ይዛ እንደቆየች የሚያስረዱ የታሪክ መዛግብት አሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ በአፍሪካ ያላት የሳሳ ታሪክ በአጭሩ እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡

2.1 ኬንያ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከ1967/68 ዓ.ም ጀምሮ በናይሮቢ አገልግሎት መስጠት ጀምራለች፡፡ በ1978 ዓ.ም የተመሠረተው የደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያንም ለምእመናን አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በስደተኞች ካምፕ የመድኃኔዓለምና ለኬንያዎች የቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በስደተኞተ ካምፕ አካባቢ እንዳለ ይነገራል፡፡

 
2.2 ሱዳን
በካርቱም ከተማ ቤተ ክርስቲያን ተቋቁማ ከ1932 ዓ.ም ጀምሮ አገል ግሎት በመስጠት ላይ ትገኛለች፡፡

2.3 ደቡብ አፍሪካ
ይህች ሀገር ከኢትዮጵያውያኑ በተጨማሪ ለኢትዮጵያና ብሔራዊት ቤተ ክርስቲያኗ ልዩ ፍቅር ያላቸውና የኢ.ኦ.ተ.ቤ. ተከታዮች ነን ብለው የሚያምኑ ሰዎች በብዛት የሚኖሩባት ናት፡፡ እነዚህ ሰዎች ይህንን እምነታቸውን በተግባር ለመተርጎም እ.ኤ.አ. ከ1872 ዓ.ም ጀምሮ እንቅስቃሴ አድርገው እ.ኤ.አ. በ1892 ዓ.ም. የተወሰኑ ምእመናን ከነበሩበት የሜቶዲስት ቤተ ክርስቲያን ተለይተው በመውጣት “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን” ብለው አቋቋሙ፡፡ ኢትዮጵያ በአድዋ ጦርነት በጣልያኖች ላይ የተቀዳጀችው የድል ዜና እንቅስቃሴያቸውን የበለጠ እንዲጎለብትና ማኅበራቸው እንዲጠናከር አድርጓል፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ በነበሩባት ውስጣዊ ችገሮች የተነሣ የፈለጉትን ያህል ልታጠናክራቸው ባትችልም አልፎ አልፎ በሚያገኙት ዕርዳታና የአይዞአችሁ መልእክት ቤተ ክርስቲያናችን በአካባቢው ላለው ሕዝብ አገልግሎት ስትሰጥ እንድትቆይ አድርጓታል፡፡ በ1993 ዓ.ም ደግሞ በስደት ወደ አካባቢ የሔዱ ኢትዮጵያውያን ምእመናን ከደቡብ አፍሪካውያኑ የእምነት ወንድሞቻቸው ጋር በመተባበር የመድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያንን አቋቁመዋል፡፡

3. አውሮፖ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ እግሯ አውሮፖን የረገጠው /በጊዜው በኢጣልያ ፍሎሬንስ በተደረገው ዓለም ዐቀፍ የአብያተ ክርስቲያናት ጉባኤ ከኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ተመርጠው በተላኩ ልኡካን አማካይነት /ከ15ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ  እንደኾነ ታሪክ እማኝነቱን ቢሰጥም በይፋ በተደራጀ መልኩ ተቋቁማ አገልግሎት መስጠት የጀመረችው በ20ኛው መቶ ክፍለ ዘመን አጋማሽ ጀምሮ ነው፡፡ በዚህ ረገድ በቀዳሚነት የሚጠቀሰው ኢትዮጵያ በፋሺስት ጣልያን በተወረረችበት ጊዜ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ወደ ሎንዶን ካደረጉት ስደት ጋር ለአጭር ጊዜም ቢሆን በተሰጠው አገልግሎት ጀምሮ በ1964 ዓ.ም በትውልደ ጃማይካውያን የቤተ ክርስቲያኗ ልጆች አማካይነት ተቋማዊ መልክ ይዞ እንዲቀጥል የተደረገው ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ በታላቋ ብሪታንያ አምስት ያህል አብያተ ክርስቲያናትና ከሦስት በላይ የጽዋ ማኅበራት ይገኛሉ፡፡

ከእንግሊዝ ቀጥሎ ቤተ ክርስቲያና ችን የደረሰችበት ሀገር ጀርመን ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በአካባቢው እንቅስቃሴ የጀመረችው በወቅቱ ለትምህርት ወደዚህ ሀገር መጥተው በነበሩት መልአከ ሰላም ዶ/ር መርዐዊ ተበጀና ዶ/ር በዕደ ማርያም አማካይነት ሲኾን በአሁኑ ወቅት ሰባት ያህል አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናትና ከሦስት የማያንሱ የጽዋ ማኅበራት ይገኛሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ከ15 ያላነሱ አብያተ ክርስቲያናት ማለትም በግሪክ /አንድ/፣ በጣልያን /ሦስት/፣ በስዊዘርላንድ /ሦስት/ በስዊድን /ሁለት/፣ በኖርዌይ /ሁለት/፣ በቤልጅየም /አንድ/፣ በኦስትርያ /አንድ/፣ በፈረንሳይ /አንድ/ አብያተ ክርስቲያናት የሚገኙ ሲሆን ወደ ቤተ ክርስቲያን ደረጃ ለማደግ ክትትል እየተደረገላቸው ያሉ ጽዋ ማኅበራት በተለያዩ የአውሮ¬ፖ ሀገራት አሉ፡፡

4. አውስትራሊያ
በዚህ አህጉር የቤተ ክርስቲያናችን እንቅስቃሴ ጥንታዊ የሚባል አይደለም፡፡ በአሁኑ ወቅት ከሦስት ያላነሱ አብያተ ክርስቲያናት የሚገኙ ሲሆን እንደዚሁ በጽዋ ማኅበርነት የተደራጁ የምእመናን ኅብረቶች አሉ፡፡

5. ሰሜን አሜሪካ
የቤተ ክርስቲያናችን የሰሜን አሜሪካ እንቅስቃሴ የተጀመረው ከ1944 ዓ.ም ጀምሮ ሲኾን ቤተ ክርስቲያን በኦፊሴል የተመሠረተችው ግን በ1951 ዓ.ም በአቡነ ቴዎፍሎስ ተባርኮ ኒውዮርክ ላይ በተቋቋመው የቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን አማካይነት ነበር፡፡ ይህ ቤተ ክርስቲያን የተቋቋመው በወቅቱ የኢትዮጵያን የጥቁር ሕዝብ አርአያነት አምነው ያስተጋቡ ለነበሩ አፍሪካ አሜሪካውያን ሲሆን ቤተ ክርስቲያኑ ቅዳሴ ቤቱ ተከብሮ በተቋቋመበት ዕለት 275 አፍሪካ አሜሪካውያን በመጠመቅ የቤተ ክርስቲያን አካል እንደሆኑ መዛግብት ያስረዳሉ፡፡ በዚህ ዓይነት በርቀት ለናፈቃት ጥቁሩ ሕዝብ ፓ-ስፊክን አቋርጣ የተቋቋመችለት ቤተ ክርስቲያን እየዋለ እያደረ በልዩ ልዩ ምክንያት ሀገሩን ትቶ ወደ አህጉሩ የሚሰደደው ሕዝብ ቁጥር እየበዛ ሲሔድ እሷም እየተስፋፋች ዛሬ ካለችበት ደረጃ ደርሳለች፡፡ በአሁኑ ወቅት በአህጉሩ ከ90 በላይ አብያተ ክርስቲያናት ይገኛሉ፡፡ 

 
6. ካናዳ
በካናዳ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የተጀመረው በቶሮንቶ ከተማ በአንድ ምእመን ድጋፍ በተገዛ ሕንፃ ውስጥ በ1964 ዓ.ም ሲሆን በአሁኑ ወቅት በመላ አህጉሩ ከሃያ አምስት በላይ አብያተ ክርስቲያናት አሉ፡፡

7. ካሪብያን ሀገሮች
በዚህ ትሪንዳድ ቶቤጎን ጉያናንና ጃማይካን በሚያጠቃልለው አካባቢ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የጀመረችው በ1964 ዓ.ም. በአባ ገብረ ኢየሱስ /በኋላ አቡነ አትናቴዎስና አቶ አበራ ጀንበሬ አማካይነት ሲኾን በአሁኑ ወቅት ከአምስት በላይ አብያተ ክርስቲያናት ይገኛሉ፡፡

8. ትሪንዳድና ቶቤጎ
ቤተ ክርስቲያን በቅኝ ገዥዎቹ በደረሰበት ተፅዕኖ በማንነት ፍለጋ ይናውዝ ለነበረው ለዚህ አካባቢ ጥቁር ሕዝብ አገልግሎት መስጠት የጀመረችው ከ1944 ዓ.ም ጀምሮ ሲሆን ከዚያ ጊዜ ጀምሮ በተደረጉ ሐዋርያዊ እንቅስቃሴዎች በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ ነፍሳት በጥምቀት ከማኅፀነ ዮርዳኖስ ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ ተወልደው በቤተ ክርስቲያን ዕቅፍ ውስጥ ገብተዋል፡፡ እየገቡም ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት በዚህ አካባቢ ከአምስት ያላነሱ አብያተ ክርስቲያናት ይገኛሉ፡፡  

9. ጃማይካ
በዚህ አካባቢ ይኖሩ የነበሩ ሕዝቦች ጣልያን ኢትዮጵያን በወረረችበት ጊዜ የነጻነታቸው ተስፋ ምድራዊ ርስት አድርገው ይቆጥሯት ለነበረችው ኢትዮጵያ አጋርነታቸውን ለማሳየት “ራስ ተፈሪያን” የሚል ቡድን መሥርተው ነበር፡፡ ንጉሡ በ1958 ዓ.ም በጃማይካ ይፋ ጉብኝት ካደረጉ በኋላ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታይ የመሆን ፍላጎት እያየለ በመምጣቱ የመጀመሪያዪቱ ቤተ ክርስቲያን በኪንግስተን ጃማይካ ተቋቋመች፡፡ ከዚያም በኋላ ግንቦት 6 ቀን 1962 ዓ.ም. ለመጀመሪያ ጊዜ ጃማይካ ሲገቡ ብሔራዊ አቀባበል በተደረገላቸው ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ አማካይነት ቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ ሐዋርያዊ አገልግሎት ሰጥታ ዛሬ ካለችበት ደረጃ ደርሳለች፡፡

II. አስተዳደራዊ መዋቅር
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከላይ በቀረበው መልኩ ዓለም ዐቀፋዊ አገልግሎት ስትሰጥ እንደየዘመኑ ሁኔታ የራሷን አስተዳደራዊ መዋቅር እየዘረጋች ሲሆን ዛሬ ባለችበት ደረጃ የዝርወት እንቅስቃሴዋን በመምራት ላይ ያለችው 12 ያህል አህጉረ ስብከትን በማቋቋም ነው፡፡ እነዚህም የመላ አፍሪካ ሀገረ ስብከት፣ የአውስትራሊያ ሀገረ ስብከት፣ የመካከለኛው ምሥራቅ ሀገረ ስብከት፣ የሰሜን ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት፣ የደቡብ ምሥራቅ አውሮፓ ሀገረ ስብከት፣ የኢየሩሳሌም ሀገረ ስብከት፣ የዲሲና አካባቢው ሀገረ ስብከት፣ የኒውዮርክና አካባቢው ሀገረ ስብከት፣ የካሪብያን ሀገራት ሀገረ ስብከትና የካናዳ ሀገረ ስብከት ናቸው፡፡

 
እዚህ ላይ ሳይጠቀስ ማለፍ የሌለበት ቤተ ክርስቲያናችን በልዩ ልዩ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት መካከል ማኅበራዊ መረዳዳትንና ቅርርብን ዓላማው አድርጎ በ1948 ዓ.ም በአምስተርዳም የተመሠረተው የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት /World Council of Cherches/ ሲመሠረት በመሳተፍ ከመሠረቱ ሀገራት አንዷ መሆኗ ነው፡፡ በተጨማሪም በአፍሪካ ደረጃ በ1963 ዓ.ም ናይሮቢ ኬንያ ላይ የተቋቋመው የአፍሪካ አብያተ ክርስቲያናት ጉባኤ መሥራች አባል ናት፡፡ ከያዝነው ርእስ አንጻር የቤተ ክርስቲያኗ የእነዚህ ጉባኤያት አባል መሆን ብዙም የጠቀማት አይመስልም፡፡ ወይም ጉባኤያቱን በአግባቡ መጠቀም አልቻለችም፡፡ 

    
III.  ችግሮች
ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዓላማዋ ሰማያዊ እንደመሆኑ በተለያዩ ጊዜያት የዓላማዋ ተፃራሪ በሆነው ዲያብሎስ ስትፈተን ኖራለች አሁንም በመፈተን ላይ ትገኛለች፡፡ በዚህ አካባቢ ያለችዋ ቤተ ክርስቲያናችንም ከምሥረ ታዋ ጀምሮ ልዩ ልዩ ችግሮች አጋጥመዋታል፡፡ ዛሬም እነዚሁ ችግሮች ሰማያዊ አገልግሎቷን በስፋት በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት አምነው በጉያዋ ለተሰበሰቡ ስዱዳን ልጆቿ እንዳትሰጥ ያደርጓታል፡፡

በአካባቢው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ያሉባትን ችግሮች ውስጣዊ እና ውጫዊ ብለን ከፍለን ማየት እንችላለን፡፡ ውስጣዊ ስንል በየደረጃው ካሉ አንዳንድ የቤተ ክርስቲያኗ አካላት፣ ካህናት፣ ምእመናን፣ ሰበካ ጉባኤያት፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ወ.ዘ.ተ.፣ የሚመጡ ችግሮችን ሲሆን ውጫዊ ስንል ደግሞ ከቤተ ክርስቲያኗ ውጭ ካሉ አካባቢያዊ ነባራዊ ሁናቴዎች የሚመጡትን ችግሮች ነው፡፡

የግእዝ ቁጥሮች አጻጻፍ

ሐምሌ 17 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ት ኑኀሚን ዋቅጅራ

የግእዝ ቋንቁ ጥንታዊያን ከተሰኙ ቋንቋዎች መካከል አንዱ ሲሆን ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት በቀን አቆጣጠርና በሥነ ጽሑፎቻቸው ሲጠቀሙበት ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲተላለፍ ቆይቷል፡፡ ዛሬም የግእዝ ቁጥሮች በኢትዮጵያውያን ዘንድ ሰፊ ሥፍራ አላቸው፡፡

በዚህ ዓምዳችን የግእዝ ቁጥሮችን አጻጻፍና የንባብ ስያሜአቸውን ማቅረባችንን እንቀጥላለን፡፡
የግእዝ ቋንቋ እንደ ማንኛውም ቋንቋ እራሱን የቻለ የቁጥር አጻጻፍ ስልቶች አሉት፡- እነዚህ ቁጥሮች እኛ በተለምዶ አጠራር የአማርኛ ቁጥሮች ብለን እንጠራቸዋለን፡፡ ይሁን እንጂ ትክክለኛውን አካሄድ ስንመለከት በአጠቃላይ የአማርኛ ብቻ ሳይሆኑ ልክ እንደ አማርኛ ፊደሎች ሁሉ ቁጥሮቹም መነሻቸው ግእዝ መሆኑን እንረዳለን፡፡

የግእዙም ሆነ አሁን እኛ የምንጠቀምበት ቁጥር ማለትም ከዐ/ዜሮ/ ጀምረን የምንጽፈው የአማርኛ ቁጥር ሳይሆን ስያሜው ከየት እንደመጣ ትክክለኛ መረጃዎች ባይኖሩም 0፣ 1፣ 2፣ 3….. እየተባሉ የሚዘረዘሩት ቁጥሮች የዐረብኛ ቁጥሮች ተብለው እንደሚጠሩ በተለያዩ መጻሕፍት ተጽፈው እናገኛለን፡፡

በኢትዮጵያ የቀን አቆጣጠር /የቀን መቁጠሪያ/ ላይ የምናገኛቸውን በየወቅቱ የሚከበሩተን ሃይማኖታዊ በዓላትንና ብሔራዊ በዓላትን ለማክበር የምጠቀመው የቀን አቆጣጠር የግእዝ ቁጥር /ኢትዮጵያዊ/ ቁጥር እንደሆኑ በግልጹ ልንረዳውና ተገቢውን ስያሜ አውቀን በስሙ ልንጠራው ይገባናል፡፡

የግእዝ ቁጥሮችን በዝርዝር ጽፈን መጨረስ ባንችልም ከብዙ በጥቂቱ በመሠረታዊነት የምንጠቀምባቸውን ቁጥሮች ከዚህ በመቀጠል እንመለከታለን፡፡

 

የግእዝ ቁጥሮች በአኀዝ

የግእዝ ቁጥሮች በፊደል

የዐረብኛ ቁጥር

አልቦ

0

አሐዱ

1

ክልኤቱ

2

ሠለስቱ

3

አርባዕቱ

4

ሐምስቱ

5

ስድስቱ

6

ስብዓቱ

7

ስመንቱ

8

ተሰዓቱ

9

አሠርቱ

10

፲፩

አሠርቱ ወአሐዱ

11

፲፪

አሠርቱ ወክልኤቱ

12

፲፫

አሠርቱ ወሠለስቱ

13

፲፬

አሠርቱ ወአርባዕቱ

14

፲፭

አሠርቱ ወሐምስቱ

15

፲፮

አሠርቱ ወስድስቱ

16

፲፯

አሠርቱ ወሰብዓቱ

17

፲፰

አሠርቱ ወስመንቱ

18

፲፱

አሠርቱ ወተሰዓቱ

19

እስራ

20

፳፩

እስራ ወአሐዱ

21

፳፪

እስራ ወክልኤቱ

22

፳፫

እስራ ወሠለስቱ

23

፳፬

እስራ ወአርባዕቱ

24

፳፭

እስራ ወሐምስቱ

25

፳፮

እስራ ወስድስቱ

26

፳፯

እስራ ወሰብዓቱ

27

፳፰

እስራ ወሰመንቱ

28

፳፱

እስራ ወተሰዓቱ

29

ሠላሳ

30

፴፩

ሠላሳ ወአሐዱ

31

፴፪

ሠላሳ ወክልኤቱ

32

፴፫

ሠላሳ ወሠለስቱ

33

፴፬

ሠላሳ ወአርባዕቱ

34

፴፭

ሠላሳ ወሐምስቱ

35

፴፮

ሠላሳ ወስድስቱ

36

፴፯

ሠላሳ ወሰብዓቱ

37

፴፰

ሠላሳ ወሰመንቱ

38

፴፱

ሠላሳ ወተሰዓቱ

39

አርብዓ

40

ሃምሳ

50

ስድሳ

60

ሰብዓ

70

ሰማንያ

80

ተሰዓ

90

ምዕት

100

፻፩

ምዕት ወአሐዱ

101

፻፪

ምዕት ወክልኤቱ

102

፻፫

ምዕት ወሠለስቱ

103

፻፬

ምዕት ወአርባዕቱ

104

፻፭

መዕት ወሐምስቱ

105

፻፮

ምዕት ወስድስቱ

106

፻፯

ምዕት ወሰብዓቱ

107

፻፰

ምዕት ወስመንቱ

108

፻፱

ምዕት ወተሰዓቱ

109

፻፲

ምዕት ወአሠርቱ

110

፻፲ወ፩

ምዕት አሠርቱ ወአሐዱ

111

፻፲ወ፪

ምዕት አሠርቱ ወክልኤቱ

112

፻፲ወ፫

ምዕት አሠርቱ ወሠለስቱ

113

፻፲ወ፬

ምዕት አሠርቱ ወአርባዕቱ

114

፻፲ወ፭

ምዕት አሠርቱ ወሐምስቱ

115

፻፲ወ፮

ምዕት አሠርቱ ወስድስቱ

116

፻፲ወ፯

ምዕት አሠርቱ ወሰብዓቱ

117

፻፲ወ፰

ምዕት አሠርቱ ወስመንቱ

118

፻፲ወ፱

ምዕት አሠርቱ ወተሰዓቱ

119

፻፳

ምዕት ወእስራ

120

፻፴

ምዕት ወሠላሳ

130

፻፵

ምዕት ወአርብዓ

140

፻፶

ምዕት ወሃምሳ

150

፻፷

ምዕት ወስድሳ

160

፻፸

ምዕት ወሰብዓ

170

፻፹

ምዕት ወሰማንያ

180

፻፺

ምዕት ወተሰዓ

190

፪፻

ክልኤቱ ምዕት

200

፪፻ወ፩

ክልኤቱ ምዕት ወአሐዱ

201

፪፻ወ፪

ክልኤቱ ምዕት ወክልኤቱ

202

፪፻ወ፫

ክልኤቱ ምዕት ወሠለስቱ

203

፪፻ወ፬

ክልኤቱ ምዕት ወአርባዕቱ

204

፪፻ወ፭

ክልኤቱ ምዕት ወሐምስቱ

205

፪፻ወ፮

ክልኤቱ ምዕት ወስድስቱ

206

፪፻ወ፯

ክልኤቱ ምዕት ወሰብዓቱ

207

፪፻ወ፰

ክለኤቱ ምዕት ወስመንቱ

208

፪፻ወ፱

ክልኤቱ ምዕት ወተሰዓቱ

209

፪፻ወ፲

ክልኤቱ ምዕት ወአሠርቱ

210

፪፻፲ወ፩

ክልኤቱ ምዕት አሠርቱ ወአሐዱ

211

፪፻፲ወ፪

ክልኤቱ ምዕት አሠርቱ ወክልኤቱ

212

፪፻፲ወ፫

ክልኤቱ ምዕት አሠርቱ ወሠልስቱ

213

፪፻፲ወ፬

ክልኤቱ ምዕት አሠርቱ ወአርባቱ

214

፪፻፲ወ፭

ክልኤቱ ምዕት አሠርቱ ወሐምስቱ

215

፪፻፲ወ፮

ክልኤቱ ምዕት አሠርቱ ወስድስቱ

216

፪፻፲ወ፯

ክልኤቱ ምዕት አሠርቱ ወሰብዓቱ

217

፪፻፲ወ፰

ክልኤቱ ምዕት አሠርቱ ወሰመንቱ

218

፪፻፲ወ፱

ክልኤቱ ምዕት አሠርቱ ወተሰዓቱ

219

፪፻፳

ክልኤቱ ምዕት ወእስራ

220

፪፻፴

ክልኤቱ ምሪዕት ወሠላሳ

230

፪፻፵

ክልኤቱ ምዕት ወአርብዓ

240

፪፻፶

ክልኤቱ ምዕት ወሃምሳ

250

፪፻፷

ክልኤቱ ምዕት ወስድሳ

260

፪፻፸

ክልኤቱ ምዕት ወሰብዓ

270

፪፻፹

ክልኤቱ ምዕት ወሰማንያ

280

፪፻፺

ክልኤቱ ምዕት ወተሰዓ

290

፫፻

ሠለስቱ ምዕት

300

፬፻

አርባዕቱ ምዕት

400

፭፻

ሐምስቱ ምዕት

500

፮፻

ስድስቱ ምዕት

600

፯፻

ስብዓቱ ምዕት

700

፰፻

ስመንቱ ምዕት

800

፱፻

ተሰዓቱ ምዕት

900

፲፻

አሠርቱ ምዕት

1000

፳፻

እስራ ምዕት

2000

፴፻

ሠላሳ ምዕት

3000

፵፻

አርብዓ ምዕት

4000

፶፻

ሃምሳ ምዕት

5000

፷፻

ሳድስ ምዕት

6000

፸፻

ሰብዓ ምዕት

7000

፹፻

ሰማንያ ምዕት

8000

፺፻

ተሰዓ ምዕት

9000

፻፻

እልፍ

10,000

፪፻፻

ክልኤቱ እልፍ

20,000

፫፻፻

ሠለስቱ እልፍ

30,000

፬፻፻

አርባዕቱ እልፍ

40,000

፭፻፻

ሐምስቱ እልፍ

50,000

፮፻፻

ስድስቱ እልፍ

60,000

፯፻፻

ሰብዓቱ እልፍ

70,000

፰፻፻

ስመንቱ እልፍ

80,000

፱፻፻

ተሰዓቱ እልፍ

90,000

፲፻፻

አሠርቱ እልፍ

100,000

፳፻፻

እስራ እልፍ

200,000

፴፻፻

ሠላሳ እልፍ

300,000

፵፻፻

አርብዓ እልፍ

400,000

፶፻፻

ሃምሳ እልፍ

500,000

፷፻፻

ስድሳ እልፍ

600,000

፸፻፻

ሰብዓ እልፍ

700,000

፹፻፻

ሰማንያ እልፍ

800,000

፺፻፻

ተሰዓ እልፍ

900,000

፻፻፻

አእላፋት

1,000,000

፲፻፻፻

ትእልፊት

10,000,000

፻፻፻፻

ትልፊታት

100,000,000

፲፻፻፻፻

ምእልፊት

1,000,000,000

 

begena 16

አቡነ ጎርጎርዮስ የሥልጠና ማእከል የበገና ተማሪዎችን አስመረቀ

ሐምሌ 17 ቀን 2005 ዓ.ም.

በታመነ ተክለ ዮሐንስ

begena 16የማኅበረ ቅዱሳን የልማት ተቋማት የአቡነ ጎርጎርዮስ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል በዜማ መሣሪያ ያሠለጠናቸውን ተማሪዎች እሑድ ሐምሌ 6 ቀን 2005 ዓ.ም አስመረቀ፡፡ ማእከሉ በመደበኛ የትምህርት መርሐ ግብሩ የአስኳላ ትምህርትን የሚሰጥ ሲሆን፤ በማታ እና በእሑድ ቅዳሜ የሥልጠና መርሐ ግብሩ ደግሞ የአብነትና የዜማ መሣሪያዎችን ሥልጠና ያካሄዳል፡፡ በያዝነው ዓመት በማታው መርሐ ግብር ለተከታታይ ዘጠኝ ወራት ሲሰጥ በነበረው የዜማ መሣሪያዎች ሥልጠና 208 ተማሪዎችን ያስመረቀ ሲሆን፤ ከነዚህ ውስጥ ከ170 በላይ የሆኑት በበገና እንዲሁም ቀሪዎቹ 30 ደግሞ በመሰንቆ የሠለጠኑ ናቸው፡፡

በተቋሙ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል ሥራ አስኪያጅ የሆኑት አቶ አብዮት እሸቱ እንደገለጹት “በትምህርት መርሐ ግብሩ የሚሰጡት የአብነት ትምህርቶች (ግዕዝና የቅዳሴ ተሰጥኦ) እንዲሁም የዜማ መሣሪያዎች (በገና፣ መሰንቆ፣ ዋሽንትና ከበሮ) ሥልጠና፤ በዋነኝነት ዓላማ አድርገው የያዙት የሠልጣኞቹን የመንፈሳዊ ሕይወት ተመስጦ ለማሳደግ ሲሆን፤ በተያያዥነትም ወደቀጣዩ ትውልድ የሚደረገውን  የመንፈሳዊ ቅርስ የቅብብል መንገድ ለማጠናከር ነው” ብለዋል፡፡ ሠልጣኞቹ ከምረቃ በኋላ በ2003 ዓ.ም በተመሠረተው የበገና ቤተሰብ ማኅበር በመታቀፍ ጥምቀትን በመሰሉ ታላላቅ መንፈሳዊና የሕዝብ ክብረ በዓላት ላይና በሌሎች ወሳኝ መድረኮች ላይ የበገና አገልግሎትን ይሰጣሉ፡፡ ይሁን እንጂ ካለው የአቅም እጥረት እና የጥያቄ ብዛት አንጻር ተመጣጣኝ የሆነ አገልግሎት ለምእመናኑም ሆነ ለቤተ ክርስቲያን ማበርከት እንዳልተቻለ አሳውቀዋል፡፡

ሥራ አስኪያጁ “የትምህርትና የሥልጠና ዘርፉን በመምህራን ከማጎልበት አንጻር የመምህራን የትምህርት ማስረጃ የተሟላ ካለመሆን የተነሣ የበገና መምህራን እጥረት የሚታይ ሲሆን፤ እንደመፍትሄ እየተወሰደ ያለ እርምጃ ቢኖር ከምሩቃን መካከል የላቀ ብቃት ያሳዩትን በመምረጥና ልዩ ሥልጠና በመስጠት ተተኪ መምህራንን የማፍራት ሥራ ነው” ብለዋል፡፡ ነገር ግን በሌሎች የዜማ ትምህርት ዘርፎች መሰል ችግሮች እንደማይታዩ ገልጸው፤ ይልቁንም ከቅዱስ ያሬድ የዜማ ትምህርት ቤት በሚወጡ መምህራን በመታገዝ ደረጃውን የጠበቀ ትምህርት እንደሚሰጥ አሳውቀዋል፡፡ ማእከሉ ከያዘው የተደራሽነት  ዓላማ አንጻር ሥልጠናውን ለማንኛውም አካል በግልጽ የሚሰጥ ሲሆን፤ እስካሁን ባለው መረጃ መሠረት አሥር ያህል የውጭ ዜጎች በበገና ላይ ያተኮረ ሥልጠና ወስደዋል፡፡

የሥልጠና ማእከሉ በቀጣይ የተደራጀ መዋቅር በመቅረጽ ከሕገ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓትና አስተምህሮ አንጻር የተፈቀዱትን የዜማ መሣሪያዎች ሥልጠና፤ የአብነት ትምህርትን በተጠናከረ መልኩ ለመቀጠልና ከተቋሙ የሚመረቁ ተማሪዎች ሕጋዊ የሆነ እውቅና እንዲያገኙ እንዲሁም ማእከሉን ወደ TVT ደረጃ ለማሳደግ ከትምህርት ሚኒስቴር እውቅናን ለመጠየቅ ተቋሙ በዝግጅት ላይ እንደሚገኝ ዋና ሥራ አስኪያጁ ገልጸዋል፡፡

በመጨረሻም ሓላፊው  ባስተላለፉት መልእክት  ሁሉም ኢትዮጵያዊ ሃይማኖትና ብሔር ሳይለይ የሀገር ቅርስ የሆነውን የበገና ትምህርት ቢማር በመጪው ትውልድ ከሚመጣ ወቀሳ መዳን እንደሚቻል ገልጸዋል፡፡

medaliya 1

ከፍተኛ ውጤት ለማስመዝገቤ ምስጢሩ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ መኖሬ ነው

ሐምሌ 5 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

ሰሞኑን ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች በመመረቅ ላይ ይገኛሉ፡፡ ከተመራቂ ተማሪዎች መካከል ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ ሁለት የወርቅ ሜዳልያዎች የተሸለመችውንmedaliya 1 አንዲት እኅት ለዛሬ እንግዳችን አድርገናታል፡፡ አንዱን የወርቅ ሜዳልያዋንም “በግቢ ጉባኤ ውስጥ በመሳተፍ በመንፈሳዊ ሕይወቴ እንድበረታና ዓላማዬን እንዳሳካ እገዛ አድርጎልኛል” ለምትለው ማኅበረ ቅዱሳን በሥጦታ አበርክታለች፡፡ የዩኒቨርስቲ ቆይታዋን፤ በግቢ ጉባኤ ውስጥ ስለነበራት ተሳትፎ እና በሌሎችም ጉዳዮች ላይ አነጋግረናታል፡፡ መልካም ቆይታ፡፡

ጥያቄ፡- ራስሽን ብታስተዋውቂን?

ፋንታነሽ ፡- ፋንታነሽ ንብረት እባላለሁ፡፡ የመጣሁት ከሚዛን ቴፒ ዩኒቨርስቲ ሚዛን ግቢ ጉባኤ ነው፡፡ የተመረቅሁት አዲስ የትምህርት ዘርፍ በሆነው በኮፕሬቲቭ አካውንቲንግ /Cooprative Accounting/ በመጀመሪያ ዲግሪ ነው፡፡

ጥያቄ፡-  ከቤተሰብ ርቀሽ ወደ ዩኒቨርስቲ መግባቱ አልከበደሽም?

 
ፋንታነሽ፡-  ወደ ዩኒቨርስቲው ስገባ ከለመድኩትና ካደግሁበት አካባቢ የተለየ ስለነበር ከብዶኛል፡፡ የገጠሙኝ ችግሮችም ነበሩ፡፡ ሴት መሆኔ፤ ለዩኒቨርስቲው አዲስ ከመሆን ጋር ተዳምሮ ብቸኝነት፤ እንዲሁም የትምህርት ቁሳቁስ ያለመሟላት ችግሮች ነበሩ፡፡ ቀስ በቀስ ለመድኩት፡፡ በእግዚአብሔር ኃይል ችግሮቹን ሁሉ መቋቋም ቻልኩ፡፡

 
ጥያቄ፡- በግቢ ጉባኤ ላይ የነበረሽ ተሳትፎ ምን ይመስል ነበር?

ፋንታነሽ፡- ወደ ዩኒቨርስቲው ስገባ በግቢ ጉባኤ ውስጥ ይሳተፉ የነበሩ የማውቃቸውን ልጆችን አገኘሁ፡፡ በግቢ ጉባኤያት  አማካይነት ከእሑድ እስከ ሰኞ የሚካሔዱትን መርሐ ግብሮች መረጃ ወሰድኩኝ፡፡ ሰዓቴን አብቃቅቼ በዚሁ መሠረት መከታተል ጀመርኩኝ፡፡ ከቤተሰቦቼ ጋር እያለሁ በሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ እሳተፍ ስለነበር ብዙም አልተቸገርኩም፡፡ ከሁለት ወራት በኋላ በአስተባባሪነትና በመዝሙር ክፍል ውስጥ በአባልነት ማገልገል ጀመርኩ፡፡ ዩኒቨርስቲ ከገባሁ በኋላ የቤተሰብ ተጽእኖ ውጪ ስለሆንኩ ራሴን በአግባቡ የመምራት ሓላፊነት ስላለብኝ ከፍተኛ ጥንቃቄ አደርግ ነበር፡፡በግቢ ጉባኤ አገልግሎትም ጥሩ ተሳታፊ ነበርኩ ማለት እችላለሁ፡፡

ጥያቄ፡- የትምህርት አቀባበልሽ እንዴት ነበር?

 
ፋንታነሽ፡-  ብዙ ማንበብ አልወድም፡፡ ትልቁ አቅሜ የነበረው በክፍል ውስጥ የነበረኝ ትምህርት የመቀበል ችሎታ ነው፡፡ በምንም ምክንያት የትምህርት ክፍለ ጊዜዬን አልቀጣም፡፡ በአግባቡም እከታተላለሁ፡፡ ከትምህርት ውጪ የማሳልፈው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ነው፡፡ ማታ ማታ በጣም ለአጭር ሰዓት የቤት ሥራዎቼን መሥራት፤ በክፍል ውስጥ ስማር ግር ያለኝ ነገር ካለ በድጋሚ መከለስ ላይ አተኩራለሁ፡፡ እንደ ሌላው ተማሪ ለረጅም ሰዓት መሸምደድ አልወድም፡፡

የመጀመሪያ ዓመት ላይ ግን ትንሽ ያነበብኩ ይመስለኛል፡፡ ግቢውን ለመላመድ፤ የአስተማሪዎቹን የትምህርት አሰጣጥና የፈተና አወጣጥ ግንዛቤ ስላልነበረኝ ይህንን ለመቋቋም በመጠኑም ቢሆን አነበብኩ፡፡ ቀሪዎቹን ዓመታት ግን ለንባብ ብዙም አልተጨነቅሁም፡፡ ተማሪ ከተማሪ በትምህርት አቀባበል ረገድ እንለያያለን፡፡ አንዳንዱ ለረጅም ሰዓት የማንበብ ልምድ ይኖረዋል፡፡ እኔ ግን ከእግዚአብሔር የተሰጠኝ ስጦታ ነው፡፡ ክፍል ውስጥ በአስተማሪዎቼ የሚሰጠውን ገለጻ በደንብ የመያዝ ብቃቱ አለኝ፡፡ ሙሉ ለሙሉ እንዳልረሳው መጠነኛ ክለሳ ብቻ ነው የማደርገው፡፡

ጥያቄ፡- ከተማሪዎች ጋር ለመላመድ አልተቸገርሽም?

ፋንታነሽ፡- የክፍለ ሀገር ልጅ ነኝ፡፡ የመጣሁት ከዳንግላ ነው፡፡ ዶርም/ማደሪያ/ የተመደብኩት ከአዲስ አበባ ልጆች ጋር ነበር፡፡ ቀስ በቀስ ለመቅረብ ጥረት አድረጌ ነበር፡፡ ዓለማዊ ፕሮግራሞች በግቢው ውስጥም ሆነ ውጪ ሲዘጋጁ አብሬያቸው እንድሔድ ይገፋፉኛል፡፡ “ሕይወት ማለት እኮ ይህ ነው” ይሉኛል፡፡ እኔ ግን በትምህርቴም ሆነ በመንፈሳዊ ሕይወቴ ስኬታማ መሆን ዋነኛው ዓላማዬ ስለነበር አሳባቸውን አልተቀበልኳቸውም፡፡ የራሴን አካሔድ በመምረጥ በእነሱ ተጽእኖ ሥር ላለመውደቅ ጥረት አደረግሁ፡፡ ቅርበቴ ሁሉ ከመንፈሳዊ እኅቶችና ወንድሞች ጋር እንዲሆን ወሰንኩ፡፡ የወሰድኩት አቋም ትክክል እንደነበር ዛሬ ላይ ሆኜ ሳስበው ያስደስተኛል፡፡ ትክክል ነበርኩ፡፡

ጥያቄ፡- እስቲ ስለ ውጤትሽ አጫውቺን?

ፋንታነሽ፡- በመጀመሪያ ዓመት ያመጣሁት ውጤት 3.98 ነበር፡፡ አንድ “B” ብቻ ነው ጣልቃ የገባው እንጂ ሁሉንም “A” ነው ያመጣሁት፡፡ በተከታታይ ዓመታት አራት ነጥብ ነው ያስመዘገብኩት፡፡ ነገር ግን በመጨረሻ ዓመት ላይ ፈተና እየወሰድን እናቴ በመታመሟ ምክንያት ከቤተሰብ እንድመጣ መልእክት ስለደረሰኝ ለዩኒቨርስቲው አስፈቅጄ ሄድኩኝ፡፡ ስመለስ ምንም ሳላጠና ተፈትኜ “B” አመጣሁ፡፡ በዚህም መሠረት ስመረቅ አጠቃላይ ውጤቴ /GPA/ 3.96 ሆነ፡፡

ጥያቄ፡- በአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት የደረጃ ተማሪ ነበርሽ?

ፋንታነሽ፡- በጭራሽ!! በአንደኛም ሆነ በሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴ የደረጃ ተማሪ አልነበርኩም፡፡ በመካከለኛ ደረጃ ላይ እገኝ ነበር፡፡ ዩኒቨርስቲ ስገባ ውስጤን በደንብ ያሳመንኩት ይመስለኛል፡፡ ዓላማዬ ስኬታማ እሆን ዘንድ ነበር ተሳካልኝ፡፡

ጥያቄ፡- በዩኒቨርስቲው ቆይታሽ ከቤተሰብ ቁጥጥር ውጪ መሆንሽ ያሳደረብሽ ተጽእኖ አልነበረም?

ፋንታነሽ፡- ከቤተሰብ ጋር ስንኖር እያንዳንዱን እንቅስቃሴያችን፤ የት ገባሽ፤ የት ወጣሽ ስለምንባል ቁጥጥሩ ይበዛል፡፡ ቁጥጥራቸው ለመልካም እንደሆነና ጥሩ ደረጃ ላይ እንድንደርስ ከማሰብ የሚመነጭ ነው፡፡ ዩኒቨርስቲ እንደምገባ ካወቅሁበት ቀን ጀምሮ ራሴን ሳዘጋጅ ነበር፡፡ ከገባሁም በኋላ በዙሪያዬ ያሉትን ፈተናዎች ለመቋቋም ጥረት አድርጌያለሁ፡፡ የቤተሰቦቼ ቁጥጥር ጠቅሞኛል እንጂ አልጎዳኝም፡፡ ተጽእኖም አልፈጠረብኝም፡፡

ጥያቄ፡- በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ውስጥ በመኖርሽ ተጠቅሜያለሁ ትያለሽ?

ፋንታነሽ፡- ቤተ ክርስቲያን ለኔ መሠረቴ ናት፡፡ እምባዬን ጠርጋልኛለች፡፡ በዩኒቨርስቲው ውስጥ የማማክረው፤ የሚደግፈኝ በሌለበት ሲጨንቀኝ፤ ዙሪያው ገደል ሲሆንብኝ ቤተ ክርስቲያን ሄጄ አለቅሳለሁ፡፡ ለእመቤቴ ጭንቀቴን ሁሉ እነግራታለሁ፡፡ መንገዴንም ቀና ታደርግልኛለች፡፡ እረጋጋለሁ፡፡ በዚህ ሁኔታ እግዚአብሔር ባይደግፈኝ ኖሮ እዚህ ደረጃ መድረስ አልችልም ነበር፡፡ በመንፈሳዊም ሆነ በስጋዊ ሕይወቴ ተጠቅሜያለሁ ማለት ይቻላል፡፡

ጥያቄ፡- በግቢ ውስጥ ትልቁ የተማሪዎች ችግር ምንድነው?

ፋንታነሽ፡- ብዙ ችግሮች አሉ፡፡ በተለይም ራስን ካለማዘጋጀት የሚመነጩ ችግሮች በቀላሉ የሚታለፉ አይደሉም፡፡ ተማሪዎች በእምነት ከማይመስላቸው ሰው ጋር ይገጥማሉ፡፡ በተለይም እህቶች ከወንዶች ጋር በሚኖራቸው ቅርበት የማንኛውም እምነት ተከታይ ይሁን እንዳልባረር ያስጠናኛል፤ ይደግፈኛል፤ ያለብኝን የፋይናንስ ችግር ያቃልልልኛል በማለት ይቀራረባሉ፡፡ ወዳልተፈለገ አቅጣጫም ያመራሉ፡፡ ሂደቱ ያስፈራል፡፡ አደርግልሻለሁ – አድርጊልኝ ወደመባባል ይደርሳሉ፡፡

ሌላው በዩኒቨርስቲ ውስጥ ጎልቶ የሚታየው ሃሜት ነው፡፡ በግቢ ጉባኤያት ውስጥ ጭምር የሚከሰት ነው፡፡ አንመካከርም፡፡ በነበርኩበት ግቢ ጉባኤ ውስጥ ትልቅ ክፍተት ነው ከምላቸው ነገሮች አንዱ ይህ ጉዳይ ነው፡፡ አንዱ አንዱን መገሰጽ ያለመቻል ችግር፡፡

ጥያቄ፡- በግቢ ጉባኤ ውስጥ የሚሰጠው ትምህርት ምን ያህል ረድቶሻል?

ፋንታነሽ፡- በግቢ ጉባኤ ውስጥ የሚሰጠው ትምህርት ጥሩ ነው፡፡ ሁሉንም ኮርሶች መጨረስ ባንቸልም ስለ እምነታችን ጥሩ ግንዛቤ የሚያስጨብጥ ነው፡፡ የማላውቀውን እንዳውቅ አድርጎኛል፡፡ በተለይም መንፈሳዊ ሕይወቴ ላይ ከፍተኛ ለውጥ እንዳመጣ ረድቶኛል፡፡ በራስ ጥረት ደግሞ ማበልጸግ፤ ማጠንከር ያስፈልጋል፡፡

ጥያቄ፡- ከወንድሞችና እህቶች ጋር የነበራችሁ ቅርበትና መደጋገፍ እንዴት ይገለጻል?

ፋንታነሽ፡- የመደጋገፍ፤ የመተባበር እንቅስቃሴዎች አሉ፡፡ አንዳችን ከተኛን ሌሎቻችን የመቀስቀስ፤ የመደጋገፍ፤ አብሮ ቤተ ክርስቲያን የመሄድ ልምዱ የዳበረ ነው፡፡
ጥያቄ፡- ከንስሀ አባቶቻችሁ ጋር ያላችሁ ቅርበት ብትገልጪልን?

ፋንታነሽ፡- ዩኒቨርስቲው በቅርቡ ከመከፈቱ አንጻር ከንስሀ አባቶቻችን ጋር የመገናኘትና የመመካከር ጥረቶች እየተደረጉ ነው፡፡ ከዚያ በፊት ግን አብረውን የነበሩ ብዙ ወንድሞችንና እህቶችን አጥተናል፡፡

ጥያቄ፡- ከፍተኛ ውጤት በማምጣትሽ ምንድነው የተሸለምሽው?

medaliyaፋንታነሽ፡- ሁለት የወርቅ ሜዳልያዎችን ነው የተሸለምኩት፡፡ አንዱ ከዩኒቨርስቲው አጠቃላይ ተመራቂዎች መካከል ከፍተኛ ነጥብ በማምጣቴ የተሸለምኩት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ከተመራቂ ሴት ተማሪዎች ከፍተኛ ነጥብ በማምጣቴ ነው፡፡

ጥያቄ፡- ከፍተኛ ውጤት ለማስመዝገብ የበቃሽበት ዋነኛ ምሥጢር ምንድነው?

ፋንታነሽ፡- የኔ ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገብ ትልቁ ምስጢር በቤተ ክርስቲያን ውስጥ መኖሬ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ለሌሎች ምሳሌ መሆን የሚችል ነው፡፡ በዩኒቨርስቲው የሚሰጠውን ትምህርት ከመንፈሳዊ ትምህርት ጋር አጣጥሞ መጓዝ እንደሚቻል የኔ ውጤት ምስክር ነው፡፡ ሌሎችንም የሚያስተምር ነው፡፡

ጥያቄ፡- ሜዳልያሽን ለማኅበረ ቅዱሳን ለመስጠት እንዴት ወሰንሽ?

ፋንታነሽ፡- ማኅበሩ የሚያከናውናቸው ተግባራት ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅሙ በመሆኑ፤ በተለይም በግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች እምነታቸውን እንዲያውቁ የሚያደርጋቸው ጥረቶች በጣም ያስደስተኛል፡፡ እኔም የዚህ ጥረት ውጤት በመሆኔ፤ ሌሎችም የኔን አርአያ እንዲከተሉ ለማድረግ ነው፡፡

ጥያቄ፡- ወደፊት ካንቺ ምን እንጠብቅ?

ፋንታነሽ፡- እድሉ ቢያጋጥመኝ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በየአመቱ የሚሰጠውን የነጻ ትምህርት እድል / /Scholarship/  ተጠቃሚ መሆን እፈልጋለሁ፡፡ በጣም እያሰብኩበት ነው፡፡ በተጨማሪም ቤተ ክርስቲያንንና አገሬን ማገልገል እፈልጋለሁ፡፡ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ውስጥ በመሳተፍ አቅሜ የሚፈቅደውን አስተዋጽኦ አደርጋለሁ፡፡ በተለይም ማኅበረ ቅዱሳን የሚያከናውናቸውን ሥራዎች ማገዝ እንዳለብኝ አምናለሁ፡፡

ጥያቄ፡- ለተማሪዎች የምታስተላልፊው መልእክት ካለሽ?

ዩኒቨርስቲ ስንገባ ማንም አያየኝም የሚል ድምዳሜ ላይ ስለምንደርስ ራሳችንን ወደፈለግነው አቅጣጫ የመምራት ነገር ይታያል፡፡ ከጓደኛ ምርጫ ጀምሮ ችግሮች ይታዩብናል፡፡ የመጣንበትን ዓላማ በመዘንጋት ደካማ ውጤት በማስመዝገብ እስከ መባረር እንደርሳለን፡፡ ከማይመስሉን ጋር በመግጠም ዳግም ልንንሳ በማንችልበት ሁኔታ አልባሌ ቦታዎች ላይ እንወድቃለን፡፡

በመጀመሪያ ደረጃ የወደፊት ህይወታችንን ለማሳካት ብለን ከቤተሰቦቻችን መለየታችንን ማሰብ ይገባናል፡፡ ዓላማችን መማር ነው፡፡ ጠንክረን በመማር የወደፊት ህይወታችንን አቅጣጫ ማስያዝ ይጠበቅብናል፡፡ የወደፊት ህይወታችን የተመሰረተው ዛሬ በምናስመዘግበው ውጤት ነው፡፡ የመጨረሻ ግባችን ምን መሆን እንዳለበት ከመጀመሪያው ውስጣችንን አሳምነን መነሳት ያስፈልጋል፡፡ ነፃነት የሚባለውን ነገር ከፈለግን ከተመረቅን በኋላ የራሳችንን ሕይወት የምንመራበት አንዱ መንገድ ስለሆነ ያኔ እንደርስበታለን፡፡ ነፃነትን እንደፈለጉ ከመሆን ጋር ማዛመድም የለብንም፡፡ ዓላማ ሊኖረን ግድ ነው፡፡

እግዚአብሔር ይስጥልኝ፡፡

እኔም እግዚአብሔር ይስጥልኝ!!

     
 
 

ብዙ ከተሰጠው ከእርሱ ብዙ ይፈለግበታል

ሐምሌ 4 ቀን 2005 ዓ.ም.

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ቤተ ክርስቲያናችን ካሏት አህጉረ ስብከት ሁሉ ለየት የሚልበት ባሕርያት አሉት፡፡ ሀገረ ስብከቱ የሀገሪቱ ዋና ከተማ እንደመሆኑ በተለያዩ ምክንያቶች ከሁሉም አህጉረ ስብከት የሚመጡ ክርስቲያኖች አገልግሎት የሚያገኙባቸው ገዳማትና አድባራት ያሉበት ሀገረ ስብከት ነው፡፡ በተለያዩ ቋንቋዎች የሚናገሩ የተለያዩ ባህሎች ያሏቸው የቤተ ክርስቲያን ቤተሰቦች ተገናኝተው በአንድነት መንፈስ አገልግሎት የሚያገኙበትና የሚቀበሉበት ሀገረ ስብከትም ነው፡፡

ሀገረ ስብከቱ በርካታ የቤተ ክርስቲያናችን መምህራን ሊቃውንት የሚገኙበትም ሀገረ ስብከት ነው፡፡ በመንፈሳዊው ትምህርት ብቻ ሳይሆን በዓለሙ የሚሰጠውን ማኅበራዊና የተፈጥሮ ሳይንስ፣ የሙያና የቀለም ትምህርቶች የተማሩ አንቱ የተባሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆችም የሚገኙበት ሀገረ ስብከት ነው፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን በታላቅ ፍቅር የሚጠብቃት፣ አገልግሎቷን ዕለት ዕለት የሚሻ ቸርና የዋህ ሕዝበ ክርስቲያን ያለበት ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ቤተ ክርስቲያን የምትተዳደርበትን ብዙ የገንዘብ የቁሳቁስና የሰው ኃይል ሀብት ይዞ የሚገኝ ነው፡፡ ከዚህም የተነሣ አርአያነት ያለው አግልግሎትን ሊሰጥም እንደሚችል የሚታሰብ ነው፡፡

እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት ሀገረ ስብከቱን ልዩ የሚያደርጉ ባሕርያቱ፤ ሀገረ ስብከቱ ያሉትን ብዙ ሀብቶች የሚያሳይ ነው፡፡ ብዙ ካለው ደግሞ ብዙ ይፈለግበታል የሚለው መጽሐፋዊ ቃል ከሀገረ ስብከቱ የምንሻውን ነገር በተሰጠው ልክ እንድንጠብቅ ያስገድዳል፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ በነገር ሁሉ ለሌሎች አህጉረ ስብከት የሚኖረውን አርአያነት፡፡

ሀገረ ስብከቱ ብዙ ገንዘብ የሚያንቀሳቅስ እንደመሆኑ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ሌሎች አህጉረ ስብከት ምሳሌ የሚሆን የገንዘብ አስተዳደርና አጠቃቀም ሥርዓት ሊኖረው ይገባል፡፡ ብዙ የገንዘብ አስተዳደር ሊቃውንት የሆኑ በርካታ የቤተ ክርስቲያን ልጆች ባለሙያዎች ያሉበት ሀገረ ስብከት በመሆኑ ቀጥሮ በማሠራትም ይሁን የነጻ አገልግሎት ሥርዓት በመዘርጋት አሠራሩን ዘመናዊ፣ ግልጽነት ያለው፣ ተጠያቂነት ያለበት፣ ለሙስና በር የማይከፍት ማድረግ ይቻለዋል፡፡ በአጠቃቀም ረገድም በግልጽነት በተሠራ ዕቅድና የዕቅድ አፈጻጸም ሥርዓት፣ አጠቃላይ አገልግሎቱን ባገናዘበ ሁኔታ፣ አሳማኝ በሆነ መንገድ ሊተገበር ይገባዋል፡፡ የንብረት አስተዳደሩም በተመሳሳይ መቃኘት ይገባዋል፡፡

ሀገረ ስብከቱ ያሉት ቅርሶች አያያዝና ጥበቃ ጉዳይም እንዲሁ መሻሻል ያለበትና በተሻለ አያያዙም ለሌሎች በቅርስ ሀብታቸው ለበለጸጉ አህጉረ ስብከት ምሳሌ ሊሆን ያስፈልጋል፡፡ ያለውን ለአገልግሎት የሚያስፈልግ የሰው ኃይልም ወጥ በሆነ ሥርዓት መምራት አለበት፡፡ አድባራትና ገዳማት ከልክ በታች ወይም ከልክ በላይ መያዝ አለመያዛቸውን፣ ለአገልግሎቱ የሚያስፈልገውን ሙያ ይዘው መገኘት አለመገኘታቸውን፣ ተገቢ እና ወጥነት ባለው የቅጥርና የዝውውር ሥርዓት እየተመራ መሆኑን፣ ከዚያ ጋር ተያይዘው የሚመጡ ሙስናና የአድልዎ አሠራሮች መኖር አለመኖራቸውን መመርመርና ማረጋገጥ ሀገረስብከቱ ወደፊት በአሠራር የለውጥ ሂደቱ ውስጥ ሊመረምራቸው የሚገቡ ነጥቦች ናቸው፡፡ በሀሜት ደረጃ የሚነሡትን የጎጠኝነት፣ የጎሰኝነት እና የቤተሰባዊ አሠራሮች መኖር አለመኖራቸውን መመርመር እንዳይከሠቱም የሚያደርግ ግልጽነት ያለው አሠራር ተግባራዊ ማድረግ ይገባል፡፡

ሀገረ ስብከቱ አርአያ ሊሆን የሚገባው በውስጥ አስተዳደራዊ ሥርዓቱ ብቻ አይደለም በስብከተ ወንጌልና በሌሎችም መንፈሳዊ አገልግሎቶችም ጭምር መሆን አለበት፡፡ በርካታ ሰባክያነ ወንጌልን ማሠልጠን፣ ማፍራት ጊዜው የሚጠይቀውን የትምህርትና ሥልጠና ዘዴዎች ተግባራዊ ለማድረግ መንቀሳቀስ አለበት፡፡ በቂና ብቁ አገልጋይ ካህናትን ማፍራት አለበት፤ ወይም ያሉትን በዚያ ደረጃ ማድረስ ይገባዋል፡፡ በዚህም ላይ ተመሥርቶ ለሃይማኖት ቤተሰቦች ለእንግዶችና መጻተኞች ተፈላጊውን የምስጢራት አገልግሎት ሊሰጥ፣ አርኪ የስብከተ ወንጌል ዐውድማ ሊሆን ይገባል፡፡ ሌሎች አህጉረ ስብከቶችንም ተንቀሳቅሰው የሚያስተምሩ የሚመክሩ ሊቃውንትን ማፍራት አለበት፡፡ ዘመናዊ የሆኑ የመገናኛ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ስብከተ ወንጌልን ማስፋፋት ይጠበቅበታል፡፡ በቂ የሚዲያ አውታሮች ያስፈልጉታል፡፡ በርካታ የብቃት ማእከሎችን ሊገነባ ይፈለግበታል፡፡

ከላይ ከተጠቀሱ መንፈሳዊ አገልግሎቶች በተጓዳኝ የልማትና ማኅበራዊ አገልግሎቶችን በማስፋፋት ለሕዝበ ክርስቲያኑም ብቻ ሳይሆን ለሀገሪቱ ዘርፈ ብዙ አስተዋጽኦ ሲያደርግ መታየት አለበት፡፡ ቢያንስ ትምህርት ቤቶችንና የሕክምና ማእከላትን ከዚህ በፊት የነበሩ መልካም ጅምሮችን መነሻ አድርጎ በዓይነት፣ በቁጥርና በጥራት ማሳደግና ማስፋፋት ከዚህ ሀገረ ስብከት በእጅጉ ይጠበቃል፡፡  

ይህ ሁሉ እንዲሆን ግን ሀገረ ስብከቱ የሚሰጣቸውን አገልግሎቶችና የአሠራር ሥርዓቱን በመላና ግምት ሳይሆን በጥናት አስደግፎ በምክክርና አሳማኝ በሆኑ አካሔዶች እንዲመራ ይጠበቅበታል፡፡ ማኅበረ ካህናቱ እርስ በእርስ የሚኖራቸው ግንኙነት ከምእመናን ጋር የሚኖራቸው ትስስር በየጊዜው ሊያድግ ሊሻሻል ይገባል፡፡ ምእመናን በሰበካ ጉባኤያት ያላቸው ተሳትፎ እንዲያድግና ቤተክርስቲያናቸውን በቅርበት የሚያገለግሉበት በቤተክርስቲያናቸው አሠራር ውስጥ አስተያየት እንዲሰጡ እንዲወስኑም ሆነው ሊታቀፉ ይገባል፡፡ በሀገረ ስብከቱ የሚገኙ ገዳማትና አድባራት ከሚታሙበት የሙስናና አድሏዊ አሠራር መጽዳት አለባቸው፡፡ አገልጋይ ካህናቱ በትምህርተ ወንጌልና በተለያዩ ዘርፈ ብዙ ሙያዎች ሊታነጹ ይገባል፡፡ ሕግ የጸናበት ሥርዓት የሚከበርበት ሀገረስብከት መሆን አለበት፡፡

ሀገረ ስብከቱ የማሻሻያ እርምጃ ለመውሰድ አሁን የጀመራቸው ጥረቶች የሚበረታቱ ናቸው፡፡ ከላይ እንደጠቀስነው በጥናትና በጥንቃቄ ለመፈጸም ጥረት የሚደረግ ከሆነ ውጤት እንደሚኖረው ይታመናል፡፡ ለዚህም የሚመለከታቸው ሁሉ ማለትም የሀገረ ስብከቱ ሠራተኞች የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች፣ ማኅበረ ካህናቱ፣ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላትና ምእመናን፤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቤተሰብ የሆኑ ሁሉ አገልግሎት ማግኛ የሆነው የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በሚፈለገው አርኪ የአገልግሎት ደረጃ ላይ እንዲደርስ የየድርሻቸውን ሊወጡ ይገባል፡፡ የማኅበረ ቅዱሳን አባላትም ሀገረስብከቱ የሚሻውን አስፈላጊ ድጋፍ ሁሉ ለማድረግ ያላቸውን ዝግጁነት ለመግለጽ ይወዳሉ፡፡

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር 

 

  • ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት 21ኛ ዓመት ቁጥር 2 ሰኔ 2005 ዓ.ም.