የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዝርወት ክፍል ሁለት

ሐምሌ 3 ቀን 2005 ዓ.ም

በዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ

ባለፈው ዕትማችን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ በዝርወት /ከኢትዮጵያ ውጪ/ ያደረገችውን ረዥም ሐዋርያዊ ጉዞ የሚዳስስ ጽሑፍ ማውጣታችን ይታወሳል፡፡ ቀጣዩን ደግሞ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡

2. አፍሪካ
የኢ.ኦ.ተ.ቤ. የጥቁሩን ሕዝብ መወከል የሚያስችላት ታሪካዊ አጋጣሚ ቢኖራትም ከዓለም ቀድማ በተመሠረተችበት አህጉር ለሚገኘው ሕዝቧ የሰጠችው አገልግሎት ሰፊ የሚባል አይደለም፡፡ እሷ አገልግሎት ባለመስጠቷ ጥቁሩ ሕዝብ ባሕሉና ልማዱ በፈጠረው ሀገረ ሰብአዊ እምነት ተይዞ ከአሚነ እግዚአብሔር ርቆ ለረጅም ዘመናት እንዲቆይ ሆኗል፡፡ አፍሪካውያን ከብዙ ሺሕ ዓመታት በኋላ ከኢትዮጵያ በእጅጉ ዘግይተው ወንጌልን የተቀበሉ አውሮ¬ውያን ያስተማሯቸውን ተቀብለዋል፡፡ ይልቁንም ቤተ ክርስቲያናችን ወደ ሕዝቡ መሔዷ ቀርቶ ራሱ ሕዝቡ እሷን ፈልጎ እንዲመጣ ኾኗል፡፡ በእርግጥ ቤተ ክርስቲያናችን ቀደም ባሉት ጊዜያት እስከ ሱዳንና ሱማልያ ተስፋ ፍታ እስልምና እስከሚቀማት ድረስ በርካታ አፍሪካውያንን በሃይማኖት ይዛ እንደቆየች የሚያስረዱ የታሪክ መዛግብት አሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ በአፍሪካ ያላት የሳሳ ታሪክ በአጭሩ እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡

2.1 ኬንያ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከ1967/68 ዓ.ም ጀምሮ በናይሮቢ አገልግሎት መስጠት ጀምራለች፡፡ በ1978 ዓ.ም የተመሠረተው የደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያንም ለምእመናን አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በስደተኞች ካምፕ የመድኃኔዓለምና ለኬንያዎች የቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በስደተኞተ ካምፕ አካባቢ እንዳለ ይነገራል፡፡

 
2.2 ሱዳን
በካርቱም ከተማ ቤተ ክርስቲያን ተቋቁማ ከ1932 ዓ.ም ጀምሮ አገል ግሎት በመስጠት ላይ ትገኛለች፡፡

2.3 ደቡብ አፍሪካ
ይህች ሀገር ከኢትዮጵያውያኑ በተጨማሪ ለኢትዮጵያና ብሔራዊት ቤተ ክርስቲያኗ ልዩ ፍቅር ያላቸውና የኢ.ኦ.ተ.ቤ. ተከታዮች ነን ብለው የሚያምኑ ሰዎች በብዛት የሚኖሩባት ናት፡፡ እነዚህ ሰዎች ይህንን እምነታቸውን በተግባር ለመተርጎም እ.ኤ.አ. ከ1872 ዓ.ም ጀምሮ እንቅስቃሴ አድርገው እ.ኤ.አ. በ1892 ዓ.ም. የተወሰኑ ምእመናን ከነበሩበት የሜቶዲስት ቤተ ክርስቲያን ተለይተው በመውጣት “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን” ብለው አቋቋሙ፡፡ ኢትዮጵያ በአድዋ ጦርነት በጣልያኖች ላይ የተቀዳጀችው የድል ዜና እንቅስቃሴያቸውን የበለጠ እንዲጎለብትና ማኅበራቸው እንዲጠናከር አድርጓል፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ በነበሩባት ውስጣዊ ችገሮች የተነሣ የፈለጉትን ያህል ልታጠናክራቸው ባትችልም አልፎ አልፎ በሚያገኙት ዕርዳታና የአይዞአችሁ መልእክት ቤተ ክርስቲያናችን በአካባቢው ላለው ሕዝብ አገልግሎት ስትሰጥ እንድትቆይ አድርጓታል፡፡ በ1993 ዓ.ም ደግሞ በስደት ወደ አካባቢ የሔዱ ኢትዮጵያውያን ምእመናን ከደቡብ አፍሪካውያኑ የእምነት ወንድሞቻቸው ጋር በመተባበር የመድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያንን አቋቁመዋል፡፡

3. አውሮፖ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ እግሯ አውሮፖን የረገጠው /በጊዜው በኢጣልያ ፍሎሬንስ በተደረገው ዓለም ዐቀፍ የአብያተ ክርስቲያናት ጉባኤ ከኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ተመርጠው በተላኩ ልኡካን አማካይነት /ከ15ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ  እንደኾነ ታሪክ እማኝነቱን ቢሰጥም በይፋ በተደራጀ መልኩ ተቋቁማ አገልግሎት መስጠት የጀመረችው በ20ኛው መቶ ክፍለ ዘመን አጋማሽ ጀምሮ ነው፡፡ በዚህ ረገድ በቀዳሚነት የሚጠቀሰው ኢትዮጵያ በፋሺስት ጣልያን በተወረረችበት ጊዜ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ወደ ሎንዶን ካደረጉት ስደት ጋር ለአጭር ጊዜም ቢሆን በተሰጠው አገልግሎት ጀምሮ በ1964 ዓ.ም በትውልደ ጃማይካውያን የቤተ ክርስቲያኗ ልጆች አማካይነት ተቋማዊ መልክ ይዞ እንዲቀጥል የተደረገው ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ በታላቋ ብሪታንያ አምስት ያህል አብያተ ክርስቲያናትና ከሦስት በላይ የጽዋ ማኅበራት ይገኛሉ፡፡

ከእንግሊዝ ቀጥሎ ቤተ ክርስቲያና ችን የደረሰችበት ሀገር ጀርመን ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በአካባቢው እንቅስቃሴ የጀመረችው በወቅቱ ለትምህርት ወደዚህ ሀገር መጥተው በነበሩት መልአከ ሰላም ዶ/ር መርዐዊ ተበጀና ዶ/ር በዕደ ማርያም አማካይነት ሲኾን በአሁኑ ወቅት ሰባት ያህል አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናትና ከሦስት የማያንሱ የጽዋ ማኅበራት ይገኛሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ከ15 ያላነሱ አብያተ ክርስቲያናት ማለትም በግሪክ /አንድ/፣ በጣልያን /ሦስት/፣ በስዊዘርላንድ /ሦስት/ በስዊድን /ሁለት/፣ በኖርዌይ /ሁለት/፣ በቤልጅየም /አንድ/፣ በኦስትርያ /አንድ/፣ በፈረንሳይ /አንድ/ አብያተ ክርስቲያናት የሚገኙ ሲሆን ወደ ቤተ ክርስቲያን ደረጃ ለማደግ ክትትል እየተደረገላቸው ያሉ ጽዋ ማኅበራት በተለያዩ የአውሮ¬ፖ ሀገራት አሉ፡፡

4. አውስትራሊያ
በዚህ አህጉር የቤተ ክርስቲያናችን እንቅስቃሴ ጥንታዊ የሚባል አይደለም፡፡ በአሁኑ ወቅት ከሦስት ያላነሱ አብያተ ክርስቲያናት የሚገኙ ሲሆን እንደዚሁ በጽዋ ማኅበርነት የተደራጁ የምእመናን ኅብረቶች አሉ፡፡

5. ሰሜን አሜሪካ
የቤተ ክርስቲያናችን የሰሜን አሜሪካ እንቅስቃሴ የተጀመረው ከ1944 ዓ.ም ጀምሮ ሲኾን ቤተ ክርስቲያን በኦፊሴል የተመሠረተችው ግን በ1951 ዓ.ም በአቡነ ቴዎፍሎስ ተባርኮ ኒውዮርክ ላይ በተቋቋመው የቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን አማካይነት ነበር፡፡ ይህ ቤተ ክርስቲያን የተቋቋመው በወቅቱ የኢትዮጵያን የጥቁር ሕዝብ አርአያነት አምነው ያስተጋቡ ለነበሩ አፍሪካ አሜሪካውያን ሲሆን ቤተ ክርስቲያኑ ቅዳሴ ቤቱ ተከብሮ በተቋቋመበት ዕለት 275 አፍሪካ አሜሪካውያን በመጠመቅ የቤተ ክርስቲያን አካል እንደሆኑ መዛግብት ያስረዳሉ፡፡ በዚህ ዓይነት በርቀት ለናፈቃት ጥቁሩ ሕዝብ ፓ-ስፊክን አቋርጣ የተቋቋመችለት ቤተ ክርስቲያን እየዋለ እያደረ በልዩ ልዩ ምክንያት ሀገሩን ትቶ ወደ አህጉሩ የሚሰደደው ሕዝብ ቁጥር እየበዛ ሲሔድ እሷም እየተስፋፋች ዛሬ ካለችበት ደረጃ ደርሳለች፡፡ በአሁኑ ወቅት በአህጉሩ ከ90 በላይ አብያተ ክርስቲያናት ይገኛሉ፡፡ 

 
6. ካናዳ
በካናዳ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የተጀመረው በቶሮንቶ ከተማ በአንድ ምእመን ድጋፍ በተገዛ ሕንፃ ውስጥ በ1964 ዓ.ም ሲሆን በአሁኑ ወቅት በመላ አህጉሩ ከሃያ አምስት በላይ አብያተ ክርስቲያናት አሉ፡፡

7. ካሪብያን ሀገሮች
በዚህ ትሪንዳድ ቶቤጎን ጉያናንና ጃማይካን በሚያጠቃልለው አካባቢ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የጀመረችው በ1964 ዓ.ም. በአባ ገብረ ኢየሱስ /በኋላ አቡነ አትናቴዎስና አቶ አበራ ጀንበሬ አማካይነት ሲኾን በአሁኑ ወቅት ከአምስት በላይ አብያተ ክርስቲያናት ይገኛሉ፡፡

8. ትሪንዳድና ቶቤጎ
ቤተ ክርስቲያን በቅኝ ገዥዎቹ በደረሰበት ተፅዕኖ በማንነት ፍለጋ ይናውዝ ለነበረው ለዚህ አካባቢ ጥቁር ሕዝብ አገልግሎት መስጠት የጀመረችው ከ1944 ዓ.ም ጀምሮ ሲሆን ከዚያ ጊዜ ጀምሮ በተደረጉ ሐዋርያዊ እንቅስቃሴዎች በብዙ ሺሕ የሚቆጠሩ ነፍሳት በጥምቀት ከማኅፀነ ዮርዳኖስ ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ ተወልደው በቤተ ክርስቲያን ዕቅፍ ውስጥ ገብተዋል፡፡ እየገቡም ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት በዚህ አካባቢ ከአምስት ያላነሱ አብያተ ክርስቲያናት ይገኛሉ፡፡  

9. ጃማይካ
በዚህ አካባቢ ይኖሩ የነበሩ ሕዝቦች ጣልያን ኢትዮጵያን በወረረችበት ጊዜ የነጻነታቸው ተስፋ ምድራዊ ርስት አድርገው ይቆጥሯት ለነበረችው ኢትዮጵያ አጋርነታቸውን ለማሳየት “ራስ ተፈሪያን” የሚል ቡድን መሥርተው ነበር፡፡ ንጉሡ በ1958 ዓ.ም በጃማይካ ይፋ ጉብኝት ካደረጉ በኋላ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታይ የመሆን ፍላጎት እያየለ በመምጣቱ የመጀመሪያዪቱ ቤተ ክርስቲያን በኪንግስተን ጃማይካ ተቋቋመች፡፡ ከዚያም በኋላ ግንቦት 6 ቀን 1962 ዓ.ም. ለመጀመሪያ ጊዜ ጃማይካ ሲገቡ ብሔራዊ አቀባበል በተደረገላቸው ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ አማካይነት ቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ ሐዋርያዊ አገልግሎት ሰጥታ ዛሬ ካለችበት ደረጃ ደርሳለች፡፡

II. አስተዳደራዊ መዋቅር
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከላይ በቀረበው መልኩ ዓለም ዐቀፋዊ አገልግሎት ስትሰጥ እንደየዘመኑ ሁኔታ የራሷን አስተዳደራዊ መዋቅር እየዘረጋች ሲሆን ዛሬ ባለችበት ደረጃ የዝርወት እንቅስቃሴዋን በመምራት ላይ ያለችው 12 ያህል አህጉረ ስብከትን በማቋቋም ነው፡፡ እነዚህም የመላ አፍሪካ ሀገረ ስብከት፣ የአውስትራሊያ ሀገረ ስብከት፣ የመካከለኛው ምሥራቅ ሀገረ ስብከት፣ የሰሜን ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት፣ የደቡብ ምሥራቅ አውሮፓ ሀገረ ስብከት፣ የኢየሩሳሌም ሀገረ ስብከት፣ የዲሲና አካባቢው ሀገረ ስብከት፣ የኒውዮርክና አካባቢው ሀገረ ስብከት፣ የካሪብያን ሀገራት ሀገረ ስብከትና የካናዳ ሀገረ ስብከት ናቸው፡፡

 
እዚህ ላይ ሳይጠቀስ ማለፍ የሌለበት ቤተ ክርስቲያናችን በልዩ ልዩ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት መካከል ማኅበራዊ መረዳዳትንና ቅርርብን ዓላማው አድርጎ በ1948 ዓ.ም በአምስተርዳም የተመሠረተው የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት /World Council of Cherches/ ሲመሠረት በመሳተፍ ከመሠረቱ ሀገራት አንዷ መሆኗ ነው፡፡ በተጨማሪም በአፍሪካ ደረጃ በ1963 ዓ.ም ናይሮቢ ኬንያ ላይ የተቋቋመው የአፍሪካ አብያተ ክርስቲያናት ጉባኤ መሥራች አባል ናት፡፡ ከያዝነው ርእስ አንጻር የቤተ ክርስቲያኗ የእነዚህ ጉባኤያት አባል መሆን ብዙም የጠቀማት አይመስልም፡፡ ወይም ጉባኤያቱን በአግባቡ መጠቀም አልቻለችም፡፡ 

    
III.  ችግሮች
ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዓላማዋ ሰማያዊ እንደመሆኑ በተለያዩ ጊዜያት የዓላማዋ ተፃራሪ በሆነው ዲያብሎስ ስትፈተን ኖራለች አሁንም በመፈተን ላይ ትገኛለች፡፡ በዚህ አካባቢ ያለችዋ ቤተ ክርስቲያናችንም ከምሥረ ታዋ ጀምሮ ልዩ ልዩ ችግሮች አጋጥመዋታል፡፡ ዛሬም እነዚሁ ችግሮች ሰማያዊ አገልግሎቷን በስፋት በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት አምነው በጉያዋ ለተሰበሰቡ ስዱዳን ልጆቿ እንዳትሰጥ ያደርጓታል፡፡

በአካባቢው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ያሉባትን ችግሮች ውስጣዊ እና ውጫዊ ብለን ከፍለን ማየት እንችላለን፡፡ ውስጣዊ ስንል በየደረጃው ካሉ አንዳንድ የቤተ ክርስቲያኗ አካላት፣ ካህናት፣ ምእመናን፣ ሰበካ ጉባኤያት፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ወ.ዘ.ተ.፣ የሚመጡ ችግሮችን ሲሆን ውጫዊ ስንል ደግሞ ከቤተ ክርስቲያኗ ውጭ ካሉ አካባቢያዊ ነባራዊ ሁናቴዎች የሚመጡትን ችግሮች ነው፡፡