p 11

ኢትዮጵያ ትሴብሕ ወትዜምር ግብፅ……

ኅዳር 10 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ማለደ ዋስይሁን

የግብ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ምርጫ ሂደት ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ምርጫ እንደ ምሳሌ

p 11

የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊን ዕረፍት ተከትሎ የግብፅ ቤተ ክርስቲያን ላለፉት ስድስት ወራት ያህል ትኩረት የሰጠችው ተተኪ ፓትርያርኳን ለመምረጥ አስፈላጊውን ሁሉ መፈጸም ላይ ነበር፡፡ የግብፅ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ወዲያ ውኑ ባደረገው ጉባኤ ለቤተ ክርስቲ ያኒቱ ዐቃቤ መንበር መሾም ሲሆን ብፁዕ አቡነ ጳኩሚስ ዘቤሔይራ ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክ ሆነው ተሰይ መዋል፡፡ ከዚያ ተከትሎ ግብፅ እግዚአብሔር ያዘዘውን ፓትርያርኳን ለማግኘት ተገቢ የምትለውን  ቀኖናዊ እርምጃዎች ሁሉ መውሰዷን ቀጠለች፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ የፓትርያርክ ምርጫ ሂደቱን ያከናወነችው እ.ኤ.አ በ1957 በወጣው ድንጋጌ መሠረት  ነው፡፡

 

የመራጮች ሁኔታ

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊን የሚተካውን ፓትርያርክ ለመምረጥ ዕድል እንዲሰጣቸው የታሰቡት መራጮች ቁጥር ከ2594 ያላነሰ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ስማቸው በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ እንዲመርጡ የታጩት 2405 ነበሩ፡፡ ቅዱስነታቸው አቡነ ሺኖዳ በ1971 ዓ.ም ሲመረጡ የተሳትፎ ዕድል ተሰጥቷቸው የነበሩት መራጮች ቁጥር 1500 ነበር፡፡ ከዚያ አንጻር ሲታይ የአሁኑ የመራጮች ቁጥር በአንድ ሺሕ ያህል ብልጫ አለው፡፡ የዚህ ምክንያት በአርባ ዓመቱ የቅዱስነታቸው የአቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ዘመን የግብፅ ቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ ዕድገትና መስፋፋት በማሳየቷ ከብዙ ከተቋቋሙ አዳዲስ አብያተ ክርስቲያናት የተወከሉ መራጮች በመታከላቸው ነው፡፡

የእነዚህ መራጮችም ዝርዝር እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር /እ.ኤ.አ/ ሐምሌ 23/ 2012 በሦስት የሀገሪቱ ጋዜጦች ይፋ ተደርጓል፡፡ በተጨማሪም በቅዱስ ማርቆስ ካቴድራል ምእመናን እንዲያገኙት ይፋ የተደረገ ሲሆን እስከ ነሐሴ 6 ድረስም ለመራጭነት በታጩት ሰዎች ማንነት ላይ የሚሰጡ አስተያየቶች ካሉ ለምርመራ እስከ ነሐሴ 6 ጊዜ ተሰጥቷል፡፡

በአጠቃላይ ሲታዩ 93 ጳጳሳት 18 ሜትሮፓሊታኖች፣ 34 መነኮሳት ተካተዋል፡፡ 1380 ምእመናን፣ የግብፅ ቤተ ክርስቲያን ጋዜጠኞች ኅብረት (Journalists’ Syndicate) አባል የሆኑ 21 ጋዜጠኞች፣ ከእነዚህ በተጨማሪም 4 የቀድሞና የአሁኑ የግብፅ ክርስቲያን የመንግሥት ሚንስትሮች፣ ክርስቲያን የፓርላማ አባላት፣ እና 27ቱ የኮፕት ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ምክር ቤት አባላት ተካተዋል፡፡ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን 5 ተወካዮች፣ ከኤርትራ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ደግሞ ቁጥራቸው በውል ያልታወቁ አባቶች ተወክለው እንደሚገኙ የወጣው ዝርዝር ያመለክታል፡፡

ከተካተቱት መራጮች 139 ሴቶች እና 29 ሴት መነኮሳት ይገኙበታል፡፡ በኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ታይቶ በማይታ ወቅ ሁኔታም ከመራጮቹ አንድ አምስተኛው መቀመጫቸው ከግብፅ ያልሆኑ ክርስቲያን ማኅበረሰቦች ሆነው ታይተዋል፡፡ በመራጮች ላይ የሚቀርቡ አቤቱታዎችን ይዞ በትክክል ያሉና የሌሉትን እንዲከታተሉ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ /Morcos/ ዘሾብራ በዐቃቤ መንበረ ፓትርያርኩ ተሰይመዋል፡፡

አሁን ተግባራዊ የተደረገው የምርጫ አካሔድ ከዚህ ቀደም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቄርሎስ ስድተኛና በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ ሲመረጡ ተግባራዊ የሆነ ነበር፡፡ አስመራጭ ኮሚቴው ሥራውን የጀመረው እ.ኤ.አ ጥቅምት 4 ቀን ነው፡፡ ሥራውንም የዐሥራ ሰባቱን ዕጩዎች ማንነት መለየት፣ ፋይልና መረጃዎችን አገላብጦ እስከ ኅዳር አጋማሽ ድረስ ለመራጮች ድምፅ አሰጣጥ የሚቀርቡትን ዕጩዎች  ማቅረብ ነው፡፡

የጾምና የጸሎት ጊዜ

የምርጫው ሂደት ያለ፤ እግዚአብሔር ረድኤት አርኪ እንደማይሆን በማመን መደረግ የሚገባቸው መንፈሳዊ ተግባራት ሁሉ ተከናውነዋል፡፡ ዋናውም ጾም ጸሎት በመሆኑ እግዚአብሔር የምርጫውን ሂደት ሁሉ እንዲመራ እርሱን መማጸን የማይረሳ ተግባር ነበር፡፡ በዚያም መሠረት አርብ እና ረቡዕ በሚጾሙበት ሥርዓት የሚጾሙ ሦስት የጾም ጊዜያት ነበሩ፡፡

የመጀመሪያው በዕጩዎች ላይ የቀረቡ አስተያየቶችን ለመመርመርና ከሰባት እስከ አምስት የሚደርሱትን ለይቶ ለማውጣት ከሚከናወነው ተግባር በፊት የሚሆንና እ.ኤ.አ ከጥቅምት 1 እስከ 3 እንዲደረግ የታቀደውና የተከናወነው ነበር፡፡ ሁለተኛው የጾም ጊዜ ደግሞ ሦስቱን አባቶች በመራጮች ድምፅ ከሚለዩበት ጊዜ በፊት ከኅዳር 19 እስከ 21 እንዲደረግ የታቀደውና የተከናወነው ነበር፡፡ ሦስተኛው ደግሞ የመሰዊያው ዕጣ አወጣጥ ሥርዓት ከመከናወኑ በፊት ከኅዳር 26 እስከ 28 እንዲደረግ የታቀደውና የተከናወነው ነበር፡፡


ዐሥራ ሰባቱ ዕጩዎች

slide_261095_1717542_freeየፓትርያርክ አስመራጭ ኮሚቴው ቅዱስነታቸው አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ በተቀበሩበት ዋዲኤል ናትሮን በሚገኘው ቅዱስ ቢሾይ ገዳም በመጓዝ ወደ ምርጫው ሂደት የሚገቡ ዕጩዎችን ለመምረጥ ጥሯል፤ በዚያ በነበረው የሁለት ሳምንት ቆይታ ባዘጋጀው የምርጫ መሥፈርትም በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት ይገባቸዋል ያላቸውን ዐሥራ ሰባት ዕጩዎች በማዘጋጀት ያላቸውን የተለያዩ ጸጋና ክህሎቶች ሲመረምር ቆይቷል፡፡ ከዚያም ዕጩዎቹ ይፋ ከተደረጉ በኋላ በእነርሱ ላይ የሚቀርቡ አስተያየትና አቤቱታዎችን ሲቀበል ሲመረምር፣ ሲወስን ቆይቷል፡፡ እነዚህ የቅሬታና የተቃውሞ አስተያየቶች የሚቀርቡት ቅዱስ ሲኖዶስ እንዲመርጡ ይፋ ካደረጋቸው መራጮች ብቻ ነበር፡፡

ለእነዚህም የተቃውሞ አቀራረቦች የዐሥራ አምስት ቀናት ጊዜ ተሰጥቷል፡፡ እነዚህም ቀናት ከጥቅምት 15 እስከ 30/2012 ያሉት ነበሩ፡፡ በግብፅ ውስጥ ካሉ ወገኖች የሚቀርቡ የተቃውሞ አስተያየቶች ለዕጩ አቅራቢ ኮሚቴው ጽሕፈት ቤት በግል በታሸገ ፖስታ እንዲቀርብ ታዟል፡፡ ከግብፅ ውጪ ካሉ ወገኖች ደግሞ በዲ ኤች ኤል ለዐቃቤ መንበረ ፓትርያርኩ በቀጥታ እንዲቀርብ ታዞ ነበር፡፡ በፖስታ የሚቀርቡ ሁሉም መልእክቶች እ.ኤ.አ ከጥቅምት 30 በፊት መላካቸውን በላያቸው ያለው ማኅተም ማመላከት ይኖርበታል፡፡

ኮሚቴውም የቀረቡትን አስተያየቶች ለመመርመር ከጥቅምት 4 ጀምሮ እንዲያከናውን ዕቅድ የወጣለት ሲሆን ያለፉትን ዕጩዎችም በኅዳር ወር የመጀመሪያና ሁለተኛ ሳምንት ውስጥ ይፋ እንዲያደርግ ሆኗል፡፡ ከእነዚህም መካከል ከ5-7 የሚደርሱ ዕጩዎችን ለይቶ ለመራጮች የድምፅ አሰጣጥ ውሳኔ ያቀርባል፡፡

በዚያም አካሔድ መሠረት ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርኩ የዐሥራ ሰባቱን ዕጩዎች ዝርዝር ይፋ አደረጉ፡፡ ከዕጩዎቹ ሰባቱ ጳጳሳት፣ ዐሥሩ ደግሞ መነኮሳት ነበሩ፡፡ ጳጳሳቱ የሚከ ተሉት ናቸው፡፡

  • ብፁዕ አቡነ ቢሾይ የቅዱስ ሲኖዶስ ጸሐፊና የዳሜይታ ሜትሮፓሊታን አንዱ ሲሆኑ በምሕንድስና ሙያ የተመረቁ ናቸው፡፡

  • ብፁዕ አቡነ ዮሐንስ የማኅበራዊ አገልግሎት ጉዳዮችን እንዲከታተሉ የተሰየሙ የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ ጸሐፊ ነበሩ፡፡ የሕክምና ትምህርትም የተከታተሉ ነበሩ፡፡

  • ብፁዕ አቡነ ቡትሮስ የብፁዕ አቡነ ሺኖዳ ልዩ ጸሐፊ ነበሩ፡፡ በግብርና ሳይንስ ዲግሪያቸውን ያገኙ ናቸው፡፡

  • ብፁዕ አቡነ ታውድሮስ የኤል ቤሔርያ ጠቅላይ ጳጳስ የሆኑና በፋርማሲ ትምህርት ከአሌክሳ ንደርያ ዩኒቨርሲቲ ተመርቀዋል፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስም አባል ናቸው፡፡

  • ብፁዕ አቡነ ራፋኤል የማእከላዊ ካይሮና ሄሊፓሊስ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ናቸው፡፡ የሕክምና ሳይንስ ትምህርት ተከታትለዋል፡፡

  • ብፁዕ አቡነ ባቭኖቲየስ የቅዱስ ሲኖዶስ አባልና የሳማልአውት እና የታሃኤል አሜኖ ጳጳስ ሲሆኑ የሕክምና ሳይንስ ምሩቅ ናቸው፡፡

  • ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ የሚላን ጳጳስና የምሕንድስና ሙያ ምሩቅ ናቸው፡፡

 

እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት ከዐሥራ ሰባቱ ዕጩዎች የጵጵስና መዓርግ ያላቸው ናቸው፡፡ የዐሥሩ መነኮሳትን ማንነት ስናይ ደግሞ የሚከተሉት ናቸው፡፡

  • አባ አንስታሲ በገዳም ያሉ መነኩሴ እና በንግድ ሥራ ሙያ ባለዲግሪ የሆኑ፣
  • አባ ማክሲሞስ በገዳም ያሉ መነኩሴና በእርሻ ሙያ ዲግሪያቸውን ያገኙ፣ በሥዕላት ዕድሳትና ጥገና ሙያ የዲፕሎማም ባለቤት የሆኑ፣
  • አባ ራፋኤል በገዳም የሚያገለግሉ መነኩሴና በሕግ ሙያ የተመረቁ፣
  • አባ ቤጉል በገዳም የሚያገለግሉ መነኩሴና በሜካኒካል ምሕንድስና ዲግሪያቸውን ያገኙ፣
  • አባ ሲኖዳ በገዳም የሚያገለግሉ መነኩሴ በሃይማኖት ጥናት ዲግሪያቸውን ያገኙ፤
  • አባ ቢሾይ በገዳም የሚያገለግሉ መነኩሴና በግብርና ዲግሪያቸውን ያገኙ፤
  • አባ ሳዊሪስ በገዳም የሚያገለግሉ መነኩሴና በሃይማኖት ጥናት ዲግሪ ያገኙ፣
  • አባ ጳኩሚስ በገዳም የሚያገለግሉ በሳይንስ እና በትምህ ርት ሙያ ዲግሪ ያላቸው፤
  • አባ ዳንኤል በገዳም የሚያገለግሉ በሳይንስ፣ በትምህርት፣ በኮፕቲክ ጥናት የዲግሪዎች ባለቤት የሆኑ፣
  • አባ ሴራፊም በገዳም የሚያገለግሉ በሳይንስ ዲግሪ ያላቸው ናቸው፡፡

በ1957 የወጣው ሕግ የሚያመለክተው ለፓትርያርክናት ዕጩ የሚቀርቡ አባቶች ዕድሜ ከአርባ የማያንስና ለዐሥራ አምስት ዓመታት በገዳማዊ ሕይወትና አገልግሎት ውስጥ ማለፍ እንደሚኖርባቸው ይደነግጋል፡፡ በመሆኑም ሁሉም ዕጩዎች ይህንን ያሟሉ ናቸው፡፡

ከዚህ በተጨማሪ ዐሥራ ሰባቱም እጩዎች ከዓለሙ ጋር ለመግባባትና ለመቅረብ የሚያስችሉ፣ ሀገራቸውንም ለማገልገል ማኅበራዊ አገልግሎቶችንና የበጐ አድራጐት ተግባራትን ማስፋፋት በሚችሉበት ሙያ ከ “ዘመናዊ” ትምህርት ቤቶች ተመርቀዋል፡፡ በገዳም አገልግሎት የተጉ፣ ምስክርነትም ያገኙ፣ ክርስቲያኖች ብቻ ሳይሆን ሌላውም የሀገሪቱ ማኅበረሰብ ዕውቅና የሰጣቸውን ተግባራት ለማከናወን እንደሚጥሩ የሚታመንባቸው ናቸው፡፡ ከእነዚህ መካከል ሀገረ ስብከት ያላቸው ዕጩዎች በተለይም ሜትሮ ፓሊታን ቢሾይ ዘዳሜታ፣ ብፁዕ አቡነ ባቭኖቲያስ ዘሳማልአውት ወታሃኤል አሜዳ፣ እና ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ዘሚላን መታጨት አነጋጋሪ ሆኖ ነበር፡፡


የአስመራጭ ኮሚቴው የመለየት ሥራ

ኮሚቴው ካቀረባቸው ዐሥራ ሰባት ዕጩዎች ከአምስት እስከ ሰባት የሚደርሱ ዕጩዎችን አወዳድሮ መለየትና ለመራጮች ድምፅ አሰጣጥ ማቅረብ ይገባው ነበር፡፡ በመሆ ኑም ዐሥራ ሰባቱን ዕጩዎች ይፋ ከተደረጉ በኋላ በዕጩዎች ላይ የሚቀርቡ ቅሬታዎችን፣ አቤቱታዎችን፣ የተለያዩ ወገኖችን አ

ስተያየት በሃይማኖት ሚዛን መመርመር ወሳኙ ተግባር ነበር፡፡ በመለየት የሥራ ሂደት የጤንነት ሁኔታ፣ የዕድሜ ሁኔታ፣ በጽሑፍ ያቀረቧቸው ሥራዎች፣ መልካም ስማቸው፣ በማኀበረሰቡ ያላቸው ተቀባይነትና ታማኝነት፣ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የነበራቸው በጐ ተጽዕኖና የፈጸሟቸው ተግባራት፣ ነገሮችን የሚያዩበት ሚዛናዊነት፣ በተለያዩ መድረኮች ያደረጓቸው የተለያዩ ገለጻዎች ሁሉ ተመርምረዋል፡፡

እጅግ አድካሚ፣ ረጅም ሂደት የነበረው፣ የኮሚቴውን ታማኝነትና ኅብረት የሚጠይቅ፣ ግልጽነት የሰፈነበት፣ ከውስጥም ከውጪም ያሉ የቤተ ክርስቲያኒቱን ሁኔታዎች ከግምት ያስገባ የመለየት ሥራ ተከናውኗል፡፡ በዩናይትድ ኪንግደም የኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጠቅላይ ጳጳስ እንደ ብፁዕ አቡነ አንጌሎስ ገለጻ መረጣው በተርታ የዲሞክራሲያዊ ምርጫ ሥርዓት ብቻ የተካሔደ ሳይሆን የጋራ ጸሎትና በእግዚአብሔር ላይ ያለ እምነትን ቅድሚያ የሚሰጥ አካሔድ ነበር፡፡

ከዚህ ሂደት በኋላ አምስት ዕጩዎች መለየታቸውን ብፁዕ አቡነ ጳኩሚስ ይፋ አደረጉ፡፡ ከእነዚህም ሁለቱ ጳጳሳት ሁለቱ መነኰሳት መሆናቸው ተረጋገጠ፡፡ አምስቱ ዕጩዎችም አባ ራፋኤል፣ ብፁዕ አቡነ ራፋኤል፣ ብፁዕ አቡነ ታውድሮስ፣ አባ ሴራፊም እና አባ ጳኩሚስ ዘአልሲሪያን ናቸው፡፡

በዚህ ሒደትም ሜትሮፓሊታን ቢሾይ፣ ብፁዕ አቡነ ዮሐንስ፣ ብፁዕ አቡነ ቡትሮስን የመሳሰሉ የተጠበቁ ታላላቅ አባቶች በዝርዝር ውስጥ ተካተው አልተገኙም፡፡ ጊዜው ግብፅ ከነበረችበት ውጥረት አንጻር የኮፕቲክ ማኀበረሰቡን ፍላጐት በሀገር ጉዳዮች በብቃት ማስጠበቅ እንዲቻል የፓትርያርክ ምርጫው እንዲፋጠን ግፊት ይደረግ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የቀድሞው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ በአገልግሎት፣ በአመራርም በግንኙነት ጉዳዮች ላይ የነበራቸው ታላቅነት ከግብፅና ከግብፅ ቤተ ክርስቲያን ወዳጆች ሁሉ ይሰጣቸው የነበረው ከበሬታ የቀጣዩን ፓትርያርክ የመለየት የምርጫ ሒደት እጅግ በጥንቃቄ የተሞላና አሳሳቢ አድርጐት ቆይቷል፡፡

 

የምርጫው ክንውን

እ.ኤ.አ ከኅዳር 19-21 ቀን 2012 ለሦስት ቀናት ጾም የታወጀ ሲሆን ከዚያ በኋላ በ24/2012 መራጮች በአስመራጭ ኮሚቴው ከተለዩት ከአም ስቱ ዕጩዎች ሦስቱን ለመለየት ድምፅ ሰጥተዋል፡፡ የመረጡትም እንዲመርጡ ተመዝግበው ከነበሩት 2405 መራጮች መካከል 2256ቱ ማለትም 93.3 /ዘጠና ሦስት ነጥብ ሦስት/ ፐርሰንቱ ነበሩ፡፡ የቀሩት በማጣራት ሂደትና በተለያዩ ምክንያቶች የቀሩ ናቸው፡፡

መራጮችም ከቀረቡላቸው አምስት ዕጩዎች ሦስቱን ብቻ የመምረጥ ሓላፊነት ተሰጥቷቸዋል፡፡ በግብፅ ያሉ መራጮች በተቆረጠው ቀን በግል ተገኝተው እንዲመርጡ ታቅዶ ነበር፡፡ ከግብፅ ውጪ ያሉት ደግሞ ወደ ግብፅ ተጉዘው በቦታው ተገኝተው እንዲመርጡ፤ አስገዳጅ ሁኔታዎች ካጋጠሙ ግን ባሉበት አስቀድመው መምረጥ የሚችሉበት ሁኔታ እንደሚመቻች ተመልክቶ ነበር፡፡ የምርጫው ወረቀት በዕጩነት የቀረቡትን የአምስቱን አባቶች ስም የያዘ ነበር፡፡

ኅዳር 24 ከተከናወነው ምርጫ በኋላ በውጤቱ ለዕጣ ሥርዓቱ የሚቀ ርቡ አባቶች ተለይተዋል፡፡ አጠቃላይ ውጤቱም ሲታይ፡-

  • ብፁዕ አቡነ ራፋኤል- 1980
  • ብፁዕ አቡነ ታውድሮስ- 1623
  • አባ ራፋኤል አቫ ሚና- 1530
  • አባ ሴራፊም አል ሶሪያ-ኒ 680
  • አባ ጳኩሚስ አል ሶሪያኒ- 305 ድምፅ አግኝተዋል፡፡

በዚህም መሠረት ለዕጣ አወጣጥ ሥርዓቱ ያለፉት አባቶች ከፍተኛ ድምፅ ያገኙት ሦስቱ ብፁዕ አቡነ ራፋኤል ብፁዕ አቡነ ታውድሮስና አባ ራፋኤል ነበሩ፡፡

ብፁዕ አቡነ ራፋኤል ከፍተኛውን ድምፅ ቁጥር ያገኙ ሲሆን ጠንካራ ሰብእና፣ ታላቅ ክብርና ዝና የነበራቸውና አወዛጋቢ ከሆኑ ነገሮች አንጻር አሉታዊ አስተያየት ያልተሰጠባቸው ነበሩ፡፡ በማእከላዊ ካይሮ ላሉ አብያተ ክርስቲያናት ረዳት ጳጳስ ሆነው እያገለገሉ ያሉና በተለይ ከወጣቶች ጋርና ከወጣቶች ጉዳይ ጳጳስ ከሆኑት አቡነ ሙሳ ጋር ቅርበት

ያላቸው ነበሩ፡፡ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቄርሎስ ስድስተኛ ጋር ቅርበት ያላቸውና ቅድምና ያላቸው በመሆኑ “ተወዳጁ አባት” ተብለው ይጠራሉ፡፡ ይሁን እንጂ በሰዎች ብቻ ሳይሆን የእግዚብሔርም ፈቃድ መኖር አለበትና ፍፃሜው በዕጣ አወጣጡ ሥርዓት ላይ ሆነ፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታውድሮስ ዳግማዊ

እ.ኤ.አ በኅዳር 4/2012 በዕለተ እሑድ ከተደረገው የቅዳሴ ሥነ ሥርዓት በኋላ የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያ ርኳን ይፋ አድርጋለች፡፡ በዚህም መሠረት ለዕጣ አወጣጥ ሥርዓቱ ተለይተው ከነበሩት ሦስቱ አባቶች መካከል ብፁዕ አቡነ ታውድሮስ ለቤተ ክርስቲያኒቱ አባት እንዲሆኑ መመ ረጣቸው ታውቋል፡፡

slide_261095_1717545_free
በዕለቱ እጅግ በርካታ የግብፅ ቤተ ክርስቲያን ቤተሰብ የሆኑ ታዋቂ ሰዎች ባለሥልጣናት ከሕፃን እስከ አዋቂ ምእመናን በተገኙበት ካይሮ በሚገኘው ታላቁ የቅዱስ ማርቆስ ካቴድራል ሥርዓተ ቅዳሴ ተከናውኗል፡፡ በቀጥታ በአልጀዚራ የአረብኛ ሥርዓተ ቅዳሴ የግብፅ ክርስቲያኖች እግዚአብሔር እርሱ ለቤተ ክርስቲያናቸው አባት አድርጐ እንዲሰጣቸው ጽኑ ተማጽኖ ላይ እንደነበሩ ከብፁዓን አባቶች ጀምሮ በሁሉም ሕዝበ ክርስቲያን ፊት ይነበብ የነበረው ስሜት ጠቋሚ ነበር፡፡

ሥርዓተ ቅዳሴውም እንዳበቃ ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርኩ ብፁዕ አቡነ ጳኩሚስ ወደ ዕጣ አወጣጥ ሥርዓቱ መሸጋገራቸውን ግልጽ አደረጉ፡፡ ያንንም ተከትሎ ዐሥራ ሁለት ሕፃናት ወደ ብፁዓን አባቶች ቀርበው ጸሎት ተደረገላቸው፡፡ ከእነዚህም ለፓትርያርክነት የተመረጠውን አባት ዕጣ ለይቶ የሚያቀርበውን ሕፃን ከእነርሱም መካከል መለየት ይገባ ነበርና፡፡ ለሕፃናቱ ዕጣ ወጥቶላቸዋል፡፡ ለዚህ ታላቅ መንፈሳዊ ሥርዓት የተመረጠው ሕፃን ቢሾይ ሆነና ወደ ዐቃቤ መንበሩ ቀረበ፡፡ በእርሳቸውም ጸሎት ከተደረገለት በኋላ ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርኩ በላዩ ቅዱሳት ሥዕላት በተሠራበት ጨርቅ የሕፃኑን ዐይኖች ሸፈኑ፡፡ ከዚያም ዕጣው ወዳለበት አቀረቡት፡፡ ታሽጎ በታቦተ ምስዋዕ ተቀምጦ ጸሎት ሲደረግበት ከነበረ የፕላስቲክ የዕጣ ጽዋ ውስጥ ለይቶ አን ዱን ዕጣ ለዐቃቤ መንበረ ፓትርያርኩ አቀረበ፡፡ ያን በጥብቅ የታሸገ ዕጣ ፈትተው ፊት ለፊት ለሚጠባበቀው የግብፅ ሕዝበ ክርስቲያን ከፍ አድርገው አሳዩ “ታውድሮስ” ተብሎ በዓረብኛ ፊደላት የተጻፈው ስም በጉልህ ይታይ ነበር፡፡ በካቴድራሉ ያለው ሕዝብ የደስታ ጩኸት አስተጋባ፡፡ ዐቃቤ መንበሩ በጉልህ ድምፅ የምስጋና ቃልን በዜማ ማሰማት ቀጠሉ፡፡ ሁሉም የእርሳቸውን ተከትሎ የምስጋናውን ቃል መመለሱን ቀጠለ፡፡ በዕጣ አወጣጥ ሥርዓቱ በሕፃን ቢሾይ ያልተነሡት ሁለት ዕጣዎች የያዙት ስም የቀሪዎቹ አባቶች መሆኑ ተረጋገጠ፡፡

 

slide_261095_1717548_freeዚያም የዓለም ሚዲያዎች ዋነኛ ትኩረት ሆኖ ዋለ፡፡ ለአራት ዐሠርት ዓመታት ያህል የግብጽን ቤተ ክርስቲያን የመሯት የፖፕ ሺኖዳ ሣልሳዊ ተተኪ ፓትርያርክ አባ ታውድሮስ መሆናቸው ተረጋገጠ፡፡ አባ ታዎድሮስ ከአባይ ዴልታ ሰሜናዊ ምዕራብ ላለው ለሰሜን ቤሄሪያ ግዛት ጠቅላይ ጳጳስ የነበሩና ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክ ለነበሩት አቡነ ጳኩሚስ ረድዕ የነበሩ ናቸው፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሉዐላዊ ሥልጣን ባለቤት የሆነው የቅዱስ ሲኖዶሱም አባል ናቸው፡፡ እ.ኤ.አ በ1952 በማንሶራህ /Mansourah/ ልዩ ስሙ ዋኒሾቢባኪ ሱሌይማን /wagihsobhybakky Suleiman/በተባለው የግብጽ አካባቢ የተወለዱ ሲሆን አባታቸው የመስኖ መሐን ዲስ የነበሩ ሲሆን የወላጅ ቤተሰባቸው በልጅነታቸው ከማንሳራ ወደ ሾሃግ ከዚያም ወደ ዳማንሆር ተዘዋውረው ይኖሩ ነበር፡፡ አባ ታዎድሮስ ጵጵስና የተቀበሉት እ.ኤ.አ በ1997 ዓ.ም ነው፡፡

አባ ታውድሮስ ከአሌክሳንደሪያ ዩኒቨርሲቲ በ1975 ዓ.ም (እ.ኤ.አ) በፋርማሲ ሙያ የመጀመሪያ ዲግሪ ያቸውን አግኝተዋል፡፡ በሲንጋፖርና በዩናይትድ ኪንግደም የፋርማሲ ምህንድስና ሙያን በአግባቡ ያጠኑ ናቸው፡፡ በ1985 በእንግሊዝም የዓለም አቀፉ የጤና ድርጅት ባዘጋጀው ፊሎሺፕ ሠልጥነዋል፡፡ ከዚያም በዳማንሆር /Damanhour/ የአንድ የመድኀኒት ኩባንያ ዳይሬክተር ነበሩ፡፡ በሌሎች በተለያዩ የግብፅ አካባቢዎች ባሉ የመድኀኒት ማምረቻ ኩባንያዎች በሓላፊነት ሠርተዋል፡፡ ስለዚህም ብቁ የአስተዳደር ችሎታ እንዳላቸው እየተጠቆመ ነው፡፡

አባ ታውድሮስ ለፖትርያርክነት ከታጩት አባቶች አንዱ ሆነው ወደ ዐሥራ ሰባቱ ዕጩዎች የገቡትም አሁን እስከ ፍጻሜው የእርሳቸው “ተወዳዳሪ” ሆነው የነበሩት ብፁዕ አቡነ ራፋኤል ጠቁመዋቸው ነው፡፡ አባ ታውድሮስ በሕዝቡ ከፍተኛ ግምት ተሰጥቷቸው በነበሩት በእኝሁ በአቡነ ራፋኤል እንደ ቅርብ ወንድም እና ባልንጀራ የሚታሰቡ ነበሩ፡፡ ከዚያም የተነሣ ለዚህ መዓርግ ሊበቁ እንደሚገባ አምነው የጠቆሟቸው መሆኑ ታውቋል፡፡ ከአቡነ ራፋኤል ሌላ ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክ የነበሩት ብፁዕ አቡነ ጳኩሚስ በቅርበት የሚያውቋቸውና የሚያከብሯቸውም ነበሩ፡፡ ታውድሮስ ውስብስብ የሆኑ የሥነ-መለኮት /theology/ ጉዳዮችን አብራርቶ በማቅረብ ጸጋቸውና ከወጣቶች ጋር በቅርበት በመሥራታቸው የታወቁ ናቸው፡፡

slide_261095_1717550_freeአባ ታውድሮስ በሀገር ውስጥ ባሉት ግብጻውያን ዘንድ ብዙ ቅርበትና ታዋቂነት ባይኖራቸውም በውጪ በስደት በሚኖሩ ግብጻውያን ክርስቲያኖች ዘንድ እጅግ ታዋቂና የተከበሩ መሆናቸው ይነገራል፡፡

በውጪ ባሉ አህጉረ ስብከቶች ያሉ አንዳንድ አባቶች “እርሳቸው ማለት የእግዚአብሔር ስጠታ ናቸው፤ ስለዚህ ተቀብለናቸዋል፤ ታውድሮስ /ቴዎድሮስ/ ማለትም ‹የእግዚብሔር ስጦታ› ማለት ነው! ስለእርሳቸው እግዚአብሔርን እናመሰግናለን” ብለዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታውድሮስ መመረጣቸውን ተከትሎ ለተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን ጋር ቃለ መጠይቅ አድርገዋል፡፡ በተለይም በግብፅ ውስጥ እየተካሔደ ካለው ፖለቲካዊ ለውጥ ጋር በተያያዘ ቤተክርስቲያኒቱ ስለሚኖራት ሚና ተደጋጋሚ ጥያቄዎች ቀርበውላቸው ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ በተለይም ፖለቲካን በተመለከተ በሰጡት ማብራሪያ “ቤተክርስቲ ያናችን በሀገር ደረጃ የምትጫወተው ሚና መንፈሳዊና ማኅበራዊ እንጂ ፖለቲካዊ አይሆንም፤ ይህ ለፖለቲካ ፓርቲዎች የተሰጠ ሚና ነው፡፡” ካሉ በኋላ አሁን በመረቀቅ ላይ ስላለው ሕገ መንግሥት በተጠየቁ ጊዜ ግን “ሕገ መንግሥቱ የሚጻፈው ከየትኛውም ሃይማኖት ወገንተኝነት በጸዳ መሆን ይገባዋል፤በሀገሪቱ ብዙኃን የሆኑትን ሙስሊሞችን ፍላጎት ብቻ የሚያስጠብቅ ማንኛውንም ሕገ መንግሥታዊ አንቀጽ ቤተ ክርስቲያን ትቃወማለች” ብለዋል፡፡ አሁን ያለውንም የግብጽ ፖለቲካ ከግምት አስገብተው ባደረባቸው ፍርሃት ምክን ያት ስለሚሰደዱ ኮፕቶች ተጠይቀው ሲመልሱ “ይህ የየግለሰቦቹ ውሳኔ ነው፤ ነገር ግን ግብጽ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የኖረባት ውድ ሀገራችን ናት፡፡ መንግሥትም ለሙስሊሙም ለክርስቲያኑም ለዜጋ ውም ሁሉ እኩል ጥበቃ ሊሰጥ ይገባል፡፡” ማለታቸውን ተገልጿል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታውድሮስ ዳግማዊ /ካልዓይ/ በታላቅ ሥነ ሥርዓት ሲመተ ፓትርያርክ ተፈጽሞላቸው 118ኛው ፓትርያርክ ሆነው በመንበረ ማርቆስ እደሚቀመጡ ተገልጿል፡፡

አባ ታውድሮስ በዐረቡ ዓለም ሰፊ፤ ነገር ግን ንዑስ /minority/ የክርስቲያን ማኀበረሰብ የሆኑትን የግብጽ ክርስቲያኖችን ለመምራት የተመረጡበት ጊዜ የግብፅ ፓለቲካ በተጋጋለበትና ከፍተኛ ጥንቃቄና ንቃት በሚጠይቅበት ወቅት በመሆኑ የወሰዱት ሓላፊነት ከባድ መሆኑን የተለያዩ መገናኛ ብዙኃን አመልክተዋል፡፡

ይህንን የአባ ታውድሮስን የግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክና የእስክንድርያ ፖፕ ሆነው መመረጣቸውን በርካታ የግብፅ ባለሥልጣናትና ታዋቂ ሰዎች በይሁንታ ተቀብለውታል፡፡ ለዚህም ጠቅላይ ሚንስትሩን ሂሻም ካንዲልን የቀደማቸው አልነበረም፡፡ ለአዲሱ ተመራጭ ፓትርያርክ “እንኳን ደስ አለዎ” ብለዋል፡፡ የጦር ሠራዊቱ አባላትና  መሪዎችም እንዲሁ መልካም የአመራር ዘመን ተመኝተውላቸዋል፡፡ የሙስሊም ወንድማማቾች ጠቅላይ መሪ ሞሐመድ ባዴ በተመሳሳይ መልካም የአስተዳደር ጊዜን ተመኝተዋል፡፡ የሙስሊም ወንድማማቾች ለነጻነትና ፍትኅ ፓርቲ /FJP/ በበኩሉ “ይህንን ምርጫ በበጎና በአድናቆት የምንመለከተው ነው፤ ከእኝህ ከአዲሱ የወንድሞቻችን የኮፕቶች መሪ ጋር ዲሞክራሲ፣ ፍትኅና እኩልነትን ለማስፋፋት አብረን እንሠራለን ሲል ያለውን በጎ አቀባበል አመልክቷል፡፡

ባለፈው ምርጫ ተወዳዳሪ ዕጩ የነበሩት ካሊድ አሊና አህመድ ሻፊቅም መልካም አስተያየቶችን ሰጥተዋል፡፡ በተለይ አሕመድ ሻፊቅ “ያለፉት አባት ፖፕ ሺኖዳ የአመራር ጊዜ መልካም ትዝታዎችን ጥሎብን አል ፏል፤ ለአባ ታውድሮስም ስኬትን እመኛለሁ” ብለዋል፡፡ ታዋቂው የዓለም አቀፉ የኔኩሌር ኢነርጂ ተቆጣጣሪ ሞሐመድ አልባራዴ፣ የአረብ ሊጉ አሚር ሙሳ ተመሳሳይ አዎንታዊ አስተያየቶችን ሰጥተዋል፡፡

 

አባ ታውድሮስ በምርጫው ከተለዩ በኋላ በዓለ ሢመቱ እስከሚፈጸም ዋዲ አል ናትሮን በሚገኘው በአባ ቢሾይ ገዳም ቆይተዋል፡፡ ከዚያም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታውድሮስ ዳግማዊ /ካልዓይ/ ኅዳር 18 2012 በታላቁ የቅዱስ ማርቆስ ካቴድራል በታላቅ ሥነ ሥርዓት ሲመተ ፓትርያርክ ተፈጽሞላቸው 118ኛው ፓትርያርክ ሆነው በመንበረ ማርቆስ መቀመጣቸው ተገልጿል፡፡

በዓለ ሢመቱም ሚትሮፖሊታን ጳኩሚስ በሚመሩት ሥርዓተ ጸሎት ተከናውኗል፡፡ ሥርዓቱ በሚያዘው መሠረትም ታውድሮስ የፖፑን አዲስ ሓላፊነቶችና የመሪነት ሚና የሚያመለክት ትልቅ ትእምርታዊ ቁልፍ ይዘው ሚትሮፖሊታኖችን፣ ጳጳሳትንና ብፁዓን የቅዱስ ሲኖዶስ አባላትን ሁሉ ከኋላ አስከትለው ወደ ካቴድራሉ ገብተዋል፡፡

ታውድሮስ በአገልግሎት ጊዜ አዲስ ነጭ ልብሰ ተክህኖ /tonia/ ለብሰው ሥርዓተ ሢመቱ ተፈጽሞላቸዋል፡፡ የኮፕቲክ ቤተ ክርስቲያን ፖፑን ዐሥራ ሦስተኛ ሐዋርያ እንደሆኑ አድርጋ ታስባለችና የዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ሥዕል የታተመበት ወርቃማ ሞጣሂት ደርበዋል፡፡ ከዚያም የፖፑን አክሊል ደፍተው በመንበረ ማርቆስ ተቀምጠዋል፡፡ ከበዓለ ሢመቱም በኋላ ተሿሚው ፖፕ ከዋና ዋና በዓላት ቀናት በስተቀር ለአንድ ዓመት እንደሚጾሙ ይጠበቃል፡፡ ስለዚህም ፖፑ “በእኩዮች መካከል በኩር” /the first among equals/ ሆኖ የቤተ ክርስቲያኒቱ መሪ ሆነው ያገለግላሉ፡፡

ለበዓለ ሢመቱ ጠቅላይ ሚንስትሩ ሂሻም ቃንዲል እና እርሳቸው የሚወክሏቸው ሌሎች ተጨማሪ ሚንስትሮችም ተጋብዘው ተገኝተዋል፡፡ ፕሬዚዳንት ሙርሲ የመገኘታቸው ነገር ግን አጠራጣሪ ሆኖ የቆየ ሲሆን እንደታሰበውም ሳይገኙ ቀርተዋል፡፡

ፓትርያርኳን ለመምረጥ በዝግጅት ላይ ያለችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተወካይ የሆኑና በብፁዕ አቡነ ናትናኤል የሚመራ የልዑካን ቡድን በእዚያ የተገኘ ሲሆን በሥርዓተ ሢመቱም በቀጥታ ተሳትፎ እንደነበራቸው አልጀዚራ የአረብኛ የቴሌቪዥን መርሐ ግብር በሰጠው ሽፋን የተገለጸ ሆኗል፡፡ የልዑካን ቡድኑ አባላት በዚያ መገኘታቸው ጠቃሚ የምርጫ ሥርዓቱን ተሞክሮዎች ማወቅና ማየት እንደሚያስችላቸው ይታመናል፡፡

የአብርሃም የይስሐቅ የያዕቆብ አምላክ /ለሕፃናት/

ኅዳር 7 ቀን 2005 ዓ.ም.

በኪዳነማርያም


አባታችን አብርሃም እግዚአብሔርን በማያውቁ፣ ጣዖት በሚያመልኩ መንደር ውስጥ ይኖር ነበር፡፡ አባቱ ጣዖት እየቀረጸ የሚሸጥ ነበር፡፡ አንድ ቀን አባቱ ሸጠህ ና! ያለውን ጣዖት ከረሀቡ ያስታግሰው ዘንድ አብላኝ ብሎ ቢጠይቀው አልሰማህ አለው፡፡ የጠየቀውን አልመልስልህ ሲለው ሰባብሮ ጣለው፡፡ ወደ ሰማይ አንጋጦ ጨረቃን ጠየቃት አልመለሰችም፣ ፀሐይን ጠየቀ አልመለሰችም፡፡ ተስፋው ሲሟጠጥ አምላከ ፀሐይ ተናበበኒ (የፀሐይ አምላክ አናገረኝ) አለ፡፡ እግዚአብሔርም ሰማው ከዘመዶችህ ተለይተህ እኔ ወደ ማሳይህ ስፍራ ውጣ አለው፡፡ አባታችን አብርሃምም እንደታዘዘው በመፈጸሙ እግዚአብሔር ቃልኪዳን ገባለት፡፡ ዘርህን እንደ ምድር አሸዋ አበዛዋለሁ የምድርም አሕዛብ ሁሉ በዘርህ ይባረካሉ አለው፡፡ አብርሃምም ከሣራ ይስሐቅን ወለደ፣ ይስሐቅም ታዛዥ ነበር፡፡ እግዚአብሔር አብርሃምን አንድያ ልጅህን ሠዋልኝ ባለው ጊዜ አብርሃም ታዘዘ፡፡ ልጁ ይስሐቅም አባቱን ታዘዘ፡፡ አምላክህን ከምታሳዝነው እኔንም ዓይን ዓይኔን እያየህ ከምትራራ በጀርባዬ ሠዋኝ ብሎ አባቱን አበረታው፡፡ እግዚአብሔርም የአብርሃምን እምነት የልጁን ታዛዥነት ዓይቶ በይስሐቅ ፋንታ ነጭ በግ በዕፀ ሳቤቅ አዘጋጅቶ እንዲሠዋ አደረገ፡፡ የበጉም ምሳሌ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡

 

ይስሐቅም ለእግዚአብሔር ታማኝ ነበር ካደገ በኋላ ርብቃን አግብቶ መንታ ልጆችን ወለደ፡፡ የልጆቹ ስም ዔሳው እና ያዕቆብ ይባላሉ፡፡ እነዚህ ልጆች ገና በእናታቸው ማኅፀን እያሉ ይገፋፉ ነበር፡፡ ነገር ግን የበኩር (የመጀመሪያ) ልጅ ሆኖ የተወለደው ኤሳው ነበር፡፡ በሀገራቸው ልማድ የበኩር ልጅ መሆን የአባትን በረከት ምርቃት የሚያሰጥ ነበር፡፡ እነዚህ ልጆች ካደጉ በኋላ ዝንባሌአቸው የተለያየ ነበር፡፡ ዔሳው አደን የሚወድ ያዕቆብም በቤት ውስጥ እናቱን የሚላላክ ሆነው አደጉ፡፡ አንድ ቀን ኤሳው ከአደን ሲመለስ ምንም አልቀናውም ነበር፡፡ በጣም ተርቦ ወንድሙ ያዕቆብን ከሠራኸው የምስር ወጥ አብላኝ አለው፡፡ ያዕቆብም ብኩርናህን ስጠኝና ከሠራሁት አበላሀለው ብሎ ነፈገው፡፡ ዔሳውም ብኲርናዬ ረኀቤን ካላስታገሰችልኝ ለችግሬ ካልሆነችኝ ለኔ ምኔ ናት ብሎ አቃለላት፣ በምስር ወጥ ሸጣት፡፡ አባታቸው ይስሐቅ ስላረጀ ምርቃቱን፣ በረከቱን ሊያስተላልፍ የበኩር ልጁ ዔሳውን ጠርቶ እነሆ እኔ አረጀሁ የምሞትበትንም ቀን አላውቅም፤ ሳልሞት ነፍሴ እንድትባርክህ የምወደውን ምግብ ሠርተህ አብላኝ አለው፡፡ ይህን ሁሉ እናታቸው ርብቃ ተደብቃ ትሰማ ነበር፡፡  አብልጣ የምትወደው ያዕቆብን ነበርና የአባቱ ምርቃት እንዳያመልጠው የሰማችውን ሁሉ ነገረችው፡፡ አባትህ የሚወደውን ምግብ እኔ አዘጋጅልሀለው አለችው፤ አባቱ እርሱ ዔሳው እንዳልሆነ ቢያውቅበት በበረከት ፈንታ መርገም እንዳይደርስበት ያዕቆብ ፈራ፡፡ አባታችሁ በእርጅና ምክንያት ዓይኑ ስለተያዘ አንተንም በመዳበስ እንዳይለይህ እንደወንድምህ ሰውነት ጠጉራም እንድትመስል በበግ ለምድ ሸፍኜ መልካሙን የዔሳው ልብስ አለብስሀለው መርገሙም በእኔ ላይ ይሁን ብላ መከረችው፣  አደፋፈረችው፡፡ ያዕቆብ እናቱ ያዘጋጀችውን ምግብ ይዞ ገባ አባዬ ያልከኝን አዘጋጅቻለሁ፤ ብላ ነፍስህም ትባርከኝ አለው፡፡ አባቱም አንተ ማነህ? ብሎ ጠየቀ፡፡ እኔ የበኩር ልጅህ ዔሳው ነኝ ብሎ ዋሸ፡፡ እንዴት ፈጥነህ አገኘህ? አለው፡፡እርሱም እግዚአብሔር አምላክህ ወደ እኔ ስላቀረበው ነው፤ አለው፡፡

 

እጁንም ዳሰሰና ድምፅህ የያዕቆብን ጠረንህ ደግሞ የዔሳውን ይመስላል ብሎ ልጁ ያዕቆብ ካቀረበለት መአድ ተመግቦ ሲጨርስ የልጁን ጠረን አሸተተ፣ እግዚአብሔር ፈቅዷልና  “እግዚአብሔርም ከሰማይ ጠል ከምድርም ስብ የእህልንም የወይንንም ብዛት ይስጥኽ፤ አሕዛብ ይገዙልህ ሕዝብም ይስገዱልህ፤ ለወንድሞችህ ጌታ ኹን የእናትህም ልጆች ይስገዱልህ፤ የሚረግምህ እርሱ ርጉም ይሁን የሚባርክህም ቡሩክ ይሁን፡፡” ብሎባረከው፡፡ ዔሳው ከአደን ደክሞ ውሎ ለአባቱ የሚሆን ምግብ አዘጋጅቶ አባዬ ያልከኝን አዘጋጅቻለሁ፤ ብላ ነፍስህም ትባርከኝ ብሎ አገባለት፡፡ አባቱም አንተ ማነህ? አለው፡፡ እኔ የበኩር ልጅህ ዔሳው ነኝ አለ፡፡ አባቱም አሁን በረከቱን የወሰደው ዔሳው አይደለምን? ወይስ ምርቃትህን ታናሽህ ያዕቆብ አታሎ ወሰደብህ? አለው፡፡ በዚህ ጊዜ ዔሳው በኀይል ጮኸ! መጀመሪያ ብኩርናዬን ቀጥሎ በረከቴን አታሎ ወሰደብኝ እያለ በጣም አዘነ፡፡ አባቱንም እንዲህ ብሎ ጠየቀው በረከትህ አንዲት ብቻ ናት? አባቱ ይሥሐቅም “እንሆ መኖሪያኽ ከምድር ስብ ከላይ ከሚገኝ ከሰማይም ጠል ይሆናል፤ በሰይፍህም ትኖራለህ ለወንድምህም ትገዛለህ፤  ነገር ግን በተቃወምኸው ጊዜ ቀንበሩን ከአንገትህ ትጥላለኽ።” አለው ዔሳውም ለእርሱ የተረፈችውን በረከት ተቀበለ፡፡ በያዕቆብም ቂም ይዞ በልቡ “ለአባቴ የልቅሶ ቀን ቀርቧል፣ ከዚያም በኋላ ወንድሜን ያዕቆብን እገድለዋለሁ!” አለ፡፡  ዔሳው የያዕቆብን ሕይወት ለማጥፋት እንደተነሳሳ እናታቸው ርብቃ በማወቋ ያዕቆብን ካደገበት ከኖረበት ቤት ወደ ካራን ምድር ወደ አጎቱ ላባ እንዲሰደድ መክራ ሸኘችው፡፡

 

በመጽሐፍ ቅዱስ በኦሪት ዘፍጥረት ላይ እንደምናነበው ያዕቆብም በእርጅናው ጊዜ ከዐሥራ ሁለቱ ልጆቹ አብልጦ ይወደው የነበረውን ዮሴፍን ወንድሞቹ ሸጠውት ሳለ ነገር ግን ክፉ አውሬ በልቶታል ብለው ዋሹት፤ በዚህም ምክንያት ለልጁ ብዙ ቀን አለቀሰ፡፡ ነገር ግን ዮሴፍ በተሰደደበት ቦታ ሁሉ እግዚአብሔር አብሮት ነበርና ኋላ ላይ ቤተሰቡ በረሀብ ምክንያት ተሰደው ወደ እርሱ በመጡ ጊዜ ለቤተሰቡ መልካም አድርጓል፡፡

 

ልጆች ከዚህ ሁሉ የምንማረው፡-

  1. ለቤተሰቦቻችን በመታዘዛችን የበለጠ እንደሚወዱን፤

  2. እናትና አባትን ማክበር እንዳለብን፤

  3. የእግዚአብሔርን በረከት ለማግኘት መጣር እንዳለብን፤

  4. የተሰጠንን ብኩርና(ሃይማኖት) ማቃለል መናቅ እንደሌለብን፤

  5. መዋሸት የሚያመጣብን መከራ ሥጋ መከራ ነፍስ እንዳለ፤

  6. እግዚአብሔር የገባውን ቃል ኪዳን እንደማያጥፍ እንደማያስቀርብን፤

  7. እግዚአብሔር የአብርሃም የይስሐቅ የያዕቆብ አምላክ ተብሎ እንዲጠራ አላፈረባቸውምና በእነዚህ ደጋግ ቅዱሳን አባቶች ምልጃ መጠቀም እንዳለብን እንማራለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን፡፡

ቤተ ጣዖቱ ተዘጋ! የቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የመሠረት ድንጋይ ተቀመጠ

ኅዳር 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

 

“በአርሲ ሀገረ ስብከት  በመርቲ ወረዳ ልዩ ስሙ ፈረቀሳ በተባለ ሥፍራ ከ120 አመታት በላይ የአርሲዋ እመቤት” በሚል የባዕድ አምልኮ ሥርዓት ሲፈጸምበት በነበረ ሥፍራ ላይ የባዕድ አምልኮ ሥርዓቱን በማጥፋት ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቅዱስ ገብርኤልን ቤተ ክርስቲያን  ለመገንባት የመሠረት ድንጋይ ኅዳር 1 ቀን 2005 ዓ.ም. አኖሩ፡፡

 

ብፁዕነታቸው በሥፍራው ለተገኙት ምእመናን በሰጡት ቃለ ምዕዳን “ከዚህ በፊት ይህ ቦታ የአርሲዋ እመቤት በሚል የዲያቢሎስ መፈንጫ፡ የሕሙማን መዋያ የነበረ ሲሆን ከአሁን በኋላ ግን የምሕረትና የፈውስ አደባባይ እንዲሁም የእግዚአብሔር ድንቅ ሥራ የሚፈጸምበት ሆኗል” ብለዋል፡፡ ለአካባቢው ምዕመናን ባስተላለፉት መልዕክትም  የቤተ ክርስቲያኑን ግንባታ በአጭር ጊዜ ውስጥ በማጠናቀቅ የተጣለባቸውን ሓላፊነት ይወጡ ዘንድ አሳስበዋል፡፡

 

ይህ የባዕድ አምልኮ ሥርዓት ከ1885 ዓ.ም. ጀምሮ ወ/ሮ ሻበሻ ወርቅ ይመር በምትባል ሴት በሥፍራው እንደተመሠረተና ምዕመናንን በማሳሳት ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን እንዲያፈነግጡ በማድረግ እስካረፈችበት እሰከ ጥቅምት 19 ቀን 1912 ዓ.ም ድረስ ቆይታለች፡፡ ነገር ግን በወቅቱ ሲከተሏትና የመሠረተችውን የባዕድ አምልኮ ሥርዓት ሲያከናውኑ የነበሩ ተከታዮቿ  “የአርሲዋ እመቤት”፤ የአካባቢው ሙስሊሞች ደግሞ “ሞሚናት” በሚል አጠራር ሥርዓቱን በማጠናከር በዚሁ ቦታ ላይ በቅዱስ ገብርኤል ስም በየዓመቱ ጥቅምት 19 እና  ግንቦት 19 ቀን በከፍተኛ ሁኔታ የባዕድ አምልኮ ሥርዓቱን ለብዙ ዘመናት ሲያከናውኑት እንደቆዩ ይነገራል፡፡

 

የብዙ ዘመናት ጸሎት ሰምሮ በብፁዕ አቡነ ናትናኤል መመሪያ ሰጪነትና ድጋፍ ሀገረ ስብከቱና የወረዳው ቤተ ክህነት እንዲሁም ምእመናን ባደረጉት ጥረት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነትና ሥርዓት መሠረት ባዕድ አምልኮ መፈጸም የተወገዘ መሆኑን በማስተማርና በማሳመን የመሠረት ድንጋዩ እንዲቀመጥና የቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን እንዲሠራ ስምምነት ላይ ተደሷርል፡፡

 

በአካባቢው የሚገኙ የእስልምና እምነት ተከታዮችም የእርሻ ማሳቸውን ለቤተ ክርስቲያን መሥሪያ በመፍቀድ ከ1200,00 ብር በላይ በማዋጣት መለገሳቸውን የደረሰን ዘገባ ያመለክታል፡፡

ራሔል እንዘ ትበኪ በእንተ ውሉዳ፥ ራሔል ስለልጆችዋ አለቀሰች

ኅዳር 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ኀይለ ኢየሱስ ቢያ

“ራሔል ስለ ልጆችዋ ስታለቅስ ብዙ ልቅሶና ዋይታ በራማ ተሰማ፤ መጽናናትንም እንቢ አለች፤ ልጆችዋ የሉምና” ማቴ.2፥18

 

ይህ የግፍ ልቅሶ 3 ጊዜ ተፈጽሟል፡፡ይኸውም፡-

1ኛ. በንጉሥ ፈርዖን ዘመን እስራኤላውያን በግብፅ እያሉ ራሔል የተባለች የሮቤል/ ስምዖን ሚስት ነፍሰጡር ሆና ጭቃ ስትረግጥ የወለደቻቸውን መንታ ልጆች ከጭቃ ጋር እንድትረግጥ ተገዳ በመርገጧ “ኢሀሎኑ በዝ ሰማይ አምላከ እስራኤል” በማለት እንባዋን ወደ ሰማይ ረጭታለች ዘዳ.1፥15፡፡ እግዚአብሔርም ልመናዋን ሰምቶ፥ ሊቀ ነቢያት ሙሴን አስነሥቶ ከግብፅ ነፃ አወጣቸው (ዘፀ. 3፥7 ተመልከቱ)

 

2ኛ. በንጉሥ ናቡከደነጾር ዘመን እስራኤላውያን በባቢሎን ተማርከው 70 ዘመን ግፍ ተፈጽሞባቸው እንደ ራሔል መሪር እንባን አልቅሰዋል፡፡ ከ70 ዘመንም በኋላ በዘሩባቤል አማካይነት ነፃ ወጥተዋል ኤር.31፥15፣ መዝ.79፥3 ተመልከቱ

 

3ኛ. ንጉሠ ነገሥት ኢየሱስ ክርስቶስ ከእመቤታችን የመወለዱን ዜና ከሰብአ ሰገል የሰማው ሄሮድስ ፥በቅንአት ሥጋዊና በፍርሃት ተውጦ፥ ጌታችንን እንዲያገኝ 144.000 ሕፃናትን ፈጅቷል፡፡ ራዕ.14፥1 በዚህም በቤተ ልሔምና በአውራጃዋ ያሉ እናቶች መሪር እንባን አሰምተው ስለነበር፥ ሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ የመከራውን ጽናት ከራሔል መከራ ጋራ አነጻጽሮ ተናገረ፡፡ ማቴ.2፥16-18 ተመልከቱ

 

ራሔል ያዕቆብን አግብታ ዮሴፍንና ብንያምን ወልዳለች፡፡ በዚህ ምክንያት የ12ቱ ነገደ እስራኤል እናት ትባላለች፡፡ በዚህ ምክንያትም፡- የእስራኤል እናቶች ተወካይ ሆና ተጠቅሳለች፡፡ ዘፍ.28፥31 ልጆች በእስራኤላውያን ዘንድ ተወዳጅ ናቸው፡፡ ስለዚህም ቅዱስ ዳዊት “ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታ ናቸው” በማለት ተናገረ፡፡ የእግዚአብሔር ስጦታ በክብር ይያዘልና፡፡ መዝ.126፥3

 

ልጅ በመወለዱ – ከድካም ያሳርፋል

  • ስም ያስጠራል
  • ዘር ይተካል
  • ወራሽ ይሆናል

 

ነቢዩ ኤርምያስ የዋይታና የመራራ ልቅሶ ድምፅ በራማ ተሰማ ራሔል ስለ ልጆችዋ አለቀሰች፤ የሉምና ስለ ልጆችዋ መጽናናትን እንቢ አለች” ያለውን /ኤር.31፥15

 

ራሔል ማን ናት? ቢሉ

1.    ራሔል ወላጅ እናታችንን ትመስላለች፡፡ ራሔል የወለደቻቸውን ልጆች በሞት እንዳጣቻቸው፤ የእኛም ወላጆች/እናቶቻችን/ ወልደውን፣ አሳድገውን፣ እናቴ አባቴ ብለን ምክራቸውን አንቀበልም ይልቁኑ እናቃልላለን፤ የሚያስፈልጋቸውን ነገር አንረዳም/መርዳት እየተቻለን የአቅማችንን እንወጣም፤ የእናትነት /የወላጅነት ክብር ነስተናቸዋል፡፡ ስለዚህ ሳንሞት በቁማችን አዝነውብናል፡፡ በዚህ ምክንያት ራሔል እያለቀሰች /እያዘነች/ ነው፡፡ የልጅ ጠባይ፣ የአናትነት ክብር ስለጠፋ “ነገር ግን በመጨረሻው ቀን የሚያስጨንቅ ዘመን እንዲመጣ ይህን እወቅ።ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱ ይሆናሉና፥ ገንዘብን የሚወዱ፥ ትምክህተኞች፥ ትዕቢተኞች፥ ተሳዳቢዎች፥ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፥ የማያመሰግኑ፥ ቅድስና የሌላቸው፥ ፍቅር የሌላቸው፥ ዕርቅን የማይሰሙ፥ ሐሜተኞች፥ ራሳቸውን የማይገዙ፥ ጨካኞች፥ መልካም የሆነውን የማይወዱ፥ ከዳተኞች፥ ችኩሎች፥ በትዕቢት የተነፉ፥ ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ ይሆናሉ፤ የአምልኮት መልክ አላቸው ኀይሉን ግን ክደዋል፤ ከእነዚህ ደግሞ ራቅ።” 2ኛ ጢሞ.3፥1-6

2.   ራሔል ሀገራችን ትመስላለች

ለምን ቢሉ የሀገር ፍቅር ስለጠፋ ነው፡፡ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ መግቢያ ላይ ስለ ሀገር ምንነት ሲገልጹ አገር ከነድንበሩ ከነፍቅሩ ስም ከነምልክቱ ከነትርጉም መረከባችንን ገልጸዋል፡፡

 

ነቢዩ ኤርምያስም “በውኑ ኢትዮጵያዊ መልኩን ወይስ ነብር ዝንጉርጉርነቱን ይለውጥ ዘንድ ይችላልን?” በማለት ይጠይቃል፣ መልሱ አይችልም ነው፡፡ አሁን አሁን ግን ብዙዎቻችን ስለ ሀገር ምንነት ያለን አመለካከት እየተዛባ ነው፡፡ ማለትም ሁሉም ሀገሬ ነው፡፡ አገር አገር አትበሉ ማለት እየተበራከተ ነው፡፡

 

ቅዱስ ዳዊት “ኢየሩሳሌም ሆይ ብረሳሽ ቀኜ ትርሳኝ ባላስብሽ፥ ምላሴ በጉሮሮዬ ይጣበቅ ከደስታዬ ሁሉ በላይ ኢየሩሳሌምን ባልወድድ” ብሏል መዝ.136፥5-6 ስለዚህ ስለሀገራችን ታሪክና ወግ፣ ባህል የማንነታችን መለያ ስለሆኑ ነገሮች ሁሉ ሊገደን ይገባል፡፡

 

3.   በሌላ በኩል ራሔል ቤተ ክርስቲያናችን እያዘነች /እያለቀሰች/ ነው፡፡ በ40 እና በ80 ቀን ከማየ ዮርዳኖስ ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ የወለደቻቸው ልጆቿ ስለጠፉ፣ የበጎ  ሃይማኖት ልጅ ስለጠፋ፣ የበጎ ሥነ ምግባር ልጅ ስለጠፋ፣ ቤተ ክርስቲያን እያዘነች ነው፡፡

 

ሁሉም እንደ ዔሳው ብኩርናውን /ልጅነቱን / ክርስትናውን ለምስር ወጥ /ለዚህ ከንቱ ዓለም/ እየሸጠ/ እየለወጠ ስለሆነ ነው፡፡ ዕብ.12፥16፣ ራዕ.3፥11፣ ምሳ.9፥1፣ ማቴ.22፥1 ይህ ሁሉ ጥሪና ግብዣ የእኛ ሆኖ ሳለ እኛ ግን የራሳችን ምኞትና ፍላጎት አሸንፎን ችላ አልነው ተውነው፡፡ በኋላ ግን ቅጣቱ የከፋ ነው፡፡

 

ስለዚህ ለሃይማኖትችን ለቤተ ክርስቲያናችን ሕግና ሥርዓት፣ ለታሪካችን ለቅርሳችን ትኩረት በመስጠት የሚጠበቅብንን አደራ ልንወጣ ይገባል፡፡ “ወዳጆች ሆይ፥ ስለምንካፈለው ስለ መዳናችን ልጽፍላችሁ እጅግ ተግቼ ሳለሁ፥ ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽሞ ስለ ተሰጠ ሃይማኖት እንድትጋደሉ እየመከርኋችሁ እጽፍላችሁ ዘንድ ግድ ሆነብኝ።” ይሁዳ 1፥3፡፡ ለዚህ ያብቃን፡፡

 

4.   ራሔል እመቤታችን ናት

እመቤታችን በራሔል የተመሰለችው፡- የሥጋ እናት ወልዳ፣ መግባ በማሳደጓ ትወደዳለች፡፡ የሃይማኖት እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ግን አባሕርያቆስ እንደ ነገረን የምንወዳት፣ እናታችን የምንላት እውነተኛ መጠጥ፣ እውነተኛ መብል ወልዳ ስለመገበችን ነው፡፡ “ኦ ማርያም በእንተዝ ናፈቅረኪ ወናዕብየኪ እስመ ወለድኪ ለነ መብልዐ ጽድቅ ዘበአማን ወስቴ ሕይወት ዘበአማን” (ቅዳሴ ማርያም)፡፡ ታዲያ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለምን አዘነች ቢሉ ሰአሊ ለነ ብሎ የሚለምን /የሚጸልይ ከፈጣሪው ጋር ስለ ኀጢአቱ ይቅርታን የሚጠቅስ ስለጠፋ ነው፡፡ እርሷ ራሷ “ከዛሬ ጀምሮ ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ይሉኛል” ሉቃ.1፥48 ብላለች ዳዊት “የምድር ባለጠጎች አሕዛብ በፊትሽ ይማልላሉ” ይላል ይለምናሉ ማለቷ ነው፡፡ መዝ.47፥12 እንኳን እመቤታችን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ ብለን ስለ ክርስቶስ እንለምናለን/ እንማልዳለን” ብሏል፡፡ 2ኛ ቆሮ.5፥20

 

ነቢዩ ኤርምያስ ራሔል ስለልጆችዋ አለቀሰች መጽናናትንም እንቢ አለች ልጆችዋ የሉምና እንዳለ፡-

ዛሬም – ወላጅ እናታችን የልጅ ጠባይ ስለጠፋ አዝናለች

  • ሀገራችን የሀገር ፍቅር ከልባችን ስለጠፋ አዝናለች

  • ቤተ ክርስቲያችን የቤተ ክርስቲያን ፍቅር ስለጠፋ አዝናለች

  • እመቤታችን የእናትነት ፍቅሯ ስለጠፋብን አዝናለች

  • መንግሥተ ሰማያት የሚወርሷት ሲጠፋ ታዝናለች፡፡

በአጠቃላይ የበጎ ሃይማኖትና ሥነ ምግባር ልጅ “ሄሮድስ” በተባለ በዚህ ከንቱ ዓለም አሳብ ጠፍተዋልና አለቀሰች አለ፡፡

 

የራሔል ልጆች ለመሆን የወጣቶች ኦርቶዶክሳዊ ግዴታ፡-

  1. በኦርቶዶክሳዊ እምነትና ምግባር፣ በሀገርና በቤተ ክርስቲያን ፍቅር በኢትዮጵያ ጨዋነትና ቁም ነገረኝነት በሰው አክባሪነትና በመንፈሳዊ ጀግንነት የአባቶችና የእናቶች አምሳያ ልጅ ሆኖ መገኘት፡፡

  2. ሲነግሩትና ሲመክሩት የሚሰማ ሲመሩት የሚከተል ክፉና ደግን ከስሕተት ሳይሆን ከአበው ምክርና ከቃለ እግዚአብሔር የሚማር ተው ሲሉት በቀላሉ የሚመለስ ሰው አክባሪና እግዚአብሔርን ፈሪ ሆኖ መገኘት፡፡

  3. ሃይማኖቱንና የቤተ ክርስቲያን አባልነቱን እየቀያየረ እንደ ዔሣው ብኩርናውን /ክብሩን/ ለምስር ወጥ የሚሸጥ አሳፋሪ ልጅ አለመሆን፡፡

  4. ከጋብቻና ከድንግልና ሕይወት ውጭ የሆነ ሌላ የክርስትና ሕይወት ስለ ሌለ የሁሉም ዓይነት ችግር መገለጫ የሆነውን 3ኛውን ዓይነት ኑሮ ላለመኖር መጠንቀቅ ወይም ከዚያ ኑሮ ፈጥኖ መውጣት፡፡

  5. የአባቶችንና የእናቶችን ኦርቶዶክሳዊ እምነትና አምልኮ በልማድ ሳይሆን በትምህርታዊ ዕውቀት በመውረስ መፈፀም፡፡

  6. በኦርቶዶክሳዊ ቋንቋ በመጸለይና በኦርቶዶክሳዊ ዜማ በመዘመር ቅዱስ መጽሐፍን በኦርቶዶክሳዊ ቋንቋ በማንበብና በመተርጐም በመማርና በማስተማር ወዘተ…. አምልኮተ እግዚአብሔርን ከልጅነት ጀምሮ መፈጸም፡፡  ማለት በዚህ ዓይነት ኦርቶዶክሳዊ እምነትና ምግባር በሰውና በእግዚአብሔር መካከል በጥበብና በሞገስ ማደግ መጎልመስ “የወይፈን በሬ” መሆን ማለት እንደ ሕፃን ሳይሆን እንደ ባለ አዕምሮ የሚያስብ “የልጅ ሽማግሌ” መሆን፡፡

  7. በዚህ ዓይነት ሕይወት ሥጋዊና ዓለማዊ የሆነውን የወጣትነት ሰውነት መንፈሳዊና ሰማያዊ ማድረግ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ወጣቶች የሚጠበቅ መንፈሳዊ ግዴታ ነው፡፡

(ፈለገ ጥበብ 2ኛ ዓመት ቁ2 መስከረም 1992)


የእግዚአብሔር ቸርነት የቅዱሳን አማላጅነት ሁላችንንም ከዚህ ክፉ ዓለም ጠብቆን ንስሐ ገብተን ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ተቀብለን የስሙ ቀዳሽ የመንግሥቱ ወራሽ ለመሆን ያብቃን፡፡

ማኅበሩ የነጻ የትምህርት ዕድል መስጠት ሊጀምር ነው፡፡

ኅዳር 5 ቀን 2005 ዓ.ም.

ዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ

 

ማኅበረ ቅዱሳን ኅዳር 2 ቀን 2005 ዓ.ም ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ተወካዮችና የማኅበረ ቅዱሳን አባላት በተገኙበት በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ በተደረገ የማስተዋወቂያ መርሐ ግብር ለአብነት ተማሪዎችና መምህራን የነጻ ትምህርት ዕድል ለመስጠት መዘጋጀቱን ገለጸ፡፡

 

በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ማኔጂንግ ዳይሬክተር ዲ/ን አዕምሮ ይኄይስ “ማኅበሩ ሐምሌ 21/2004 ዓ.ም በአዲስ አበባ ግዮን ሆቴል ከአብነት ምስክርና ከዩኒቨርስቲ ምሁራን ጋር የዘመናዊውን ትምህርት ከአብነት ትምህርት ጋር አቀዳጅቶ የመስጠትን አስፈላጊነት ወሳኝ ውይይት አድርጎ፤ በአባ ጊዮርጊስ ስም የተሰየመ ነጻ የትምህርት ዕድል ማዘጋጀቱን” ገልጸዋል፡፡

 

የአብነት ትምህርት ማጠናከሪያ፣ ማቋቋሚያና የአባ ጊዮርጊስ የነጻ ትምህርት ሥልጠና ዕድልን በተመለከተ አጠቃላይ ገለጻ ያደረጉት፤ የቅዱሳት መካናትና ልማት የቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ “የመርሐ ግብሩ ዓላማ የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ዘመኑን በዋጀ መልኩ ተጽዕኖ ፈጣሪ የሚያደርጋቸው ነው” ብለዋል፡፡ እንደ ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ ገለጻ የአባ ጊዮርጊስ ነጻ ትምህርት ዕድል የአብነት ትምህርት ተማሪዎችና መምህራን ከመለስተኛ ደረጃ እስከ ከፍተኛ የዘመናዊ ትምህርት ወይም ሥልጠና እንዲያገኙ የሚያግዝ ዕቅድ ነው፡፡ አክለውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ቤቶች ከዘመናዊው ትምህርት ጋር አብሮ አላደገም ያሉት ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ በዚህም እነዚህ ትምህርት ቤቶች ያለተንከባካቢና ከመንግሥት የሚደረገው ድጎማ መቅረቱ ሊቃውንቱ ያለተተኪ እንዲቀሩ አድርጓቸዋል፤ በዚህም ገዳማት ችግር ላይ መውደቃውቸን ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም የአብነት ትምህርት እንደ ዕውቀት ተመራጭ አለመሆኑ፣ የአብነት ትምህርት ውሱንነት፣ በአብነት ትምህርት ለተማሩ አማራጭ የሥራ ዕድል አለመኖሩና ዘመኑን በዋጀ ሁኔታ በየደረጃው በበቂ ዕውቀት የሚያገለግሉ ካህናት ማነስን እንደ ችግር የጠቀሱት ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ፤ ይህ መርሐ ግብር ለቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ቤቶች የሰው ኀይል ምንጭ በመሆናቸው አስፈላጊ ነው ብለዋል፡፡

 

መርሐ ግብሩ በ750 ተማሪዎች ለሁለት ዓመት በሚቆይ የሙከራ ጊዜ የሚጀመር ሲሆን በዓመት እስከ አምስት ሚሊዮን ብር የሚጠይቅና በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር የሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን የገንዘብ ምንጭ መሆናቸውን እንዲሁም በጥር 2005 ዓ.ም እንደሚጀመር ለማወቅ ተችሏል፡፡

7

ቅዱስ ዑራኤል በግሸን አምባ

ጥቅምት 29 ቀን 2005 ዓ.ም.

መምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

  • ‹‹መስቀሉ በአዳል ሜዳ በር  እንዲገባ ያመላከተው ቅ/ ዑራኤል ነው››
  • ‹‹ጥር 22 ቀን ቤተ ክርስቲያኑ ይመረቃል››

 

ቅዱስ ተብለው የሚጠሩት ደገኛው ንጉሠ ነገሥት ዐፄ ካሌብ የሀገረ ናግራን ክርስቲያኖችን ለመታደግ ዘምተው የአሕዛቡን ንጉሥ ፊንሀስን ድል አድርገው ሲመለሱ በነበራቸው መንፈሳዊ ፀጋ እንዲሁም በአበ ነፍሳቸው ፈቃደ ክርስቶስ  ምክር የግሸን ደብረ ከርቤን ክብር በመረዳት ፤በ517 ዓ.ም ታቦተ እግዚአብሔር አብንና ታቦተ ማርያምን ከሀገረ ናግራን ወደ ኢትዮጵያ በማምጣት በግሸን አምባ ላይ ቤተ መቅደስ ሠርተው ቀዳሽና አወዳሽ መድበው ደብረዋታል፡፡ በወቅቱም አምባው መግቢያ ካለመኖሩ የተነሣ ተራራውን ሲዞሩ የንብ መንጋ በማየታቸው “አምባ አሰል” ብለውታል፡፡ ትርጓሜውም የማር አምባ ማለት ነው፡፡ በዚህ ምክንያት አካባቢው አምባ ሰል ሲባል ይኖራል፡፡

 

የግሸን አምባ ቀደሞ በቅዱሳን ስትገለገል የነበረች በመሆኗ በተለያዩ ጊዜያት ነገሥታት፣ የነገሥታት ቤተሰቦች ጎብኝተዋታል፡፡ ሥርዓተ ቤተክርስቲያንና ሥርዓተ ንግሥና ተምረውባታል፡፡ ከዚህም የተነሣ ስመ ታፍልሶ ገጥሟታል፡፡ በዐፄ ድልነአድ ዘመነ መንግሥት በ866 ዓ.ም ደብረ ነጎድጓድ በ11ኛው ክፍለ ዘመን በኢትዮጵያ ነግሦ የነበረውና በሕንፃ ቤተ ክርስቲያን አናፂነቱ የሚታወቀው ንጉሥ ላልይበላ ከቦታው ደርሶ ቤተመቅደስ ለመሥራት ሲጀምር ‹‹ከዚህ ቦታ ላይ ቤተ ክርስቲያን የምታነጸው አንተ ሳትሆን ዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ ነው፡፡›› ተብሎ በህልሙ ስለተነገረው፤ በሀገሩ በላልይበላ የእግዚብሔር አብ ቤተመቅደስን ሠርቶ ስለነበር ‹‹ደብረ እግዚአብሔር›› ብሎ ሰየመው፡፡ ብዙም ሳይቆይ ነገሥታቱ ይማጸኑበት የክብርና የማዕረግ ዕቃዎችን ያስቀምጡበትና ይማሩበት ስለነበር ‹‹ደብረ ነገሥት›› ተባለች፡፡

 

በ1446 ዓ.ም ዕቅበተ እምነትን ከንግሥና አስተባብረው የያዙት ዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ ከአባታቸው ዐፄ ዳዊት ድንገተኛ ዕረፍት በኋላ ኢትዮጵያን እንዲያስተዳድሩ ሥልጣነ መንበሩን በመያዛቸው ቀድሞ ለአባታቸው ተሰጥቶ የነበረውን የአምላካችን የኢየሱስ ክርስቶስ ክቡር መስቀል ተረከበው ‹‹መስቀሌን በመስቀለኛ ቦታ አኑር›› ተብለው በተሰጣቸው ትእዛዝ መሠረት መስቀሉን በመስቀለኛ ቦታ ለማሳረፍ ሱባኤ በመያዝ ጸሎተ ምህላ በማድረግ መስቀሉን ይዘው ኢትዮጵያን መዞር ጀመሩ ኋላም ፤ የመስቀሉን ማረፊያ መስቀለኛውን ቦታ ግሸን አምባን  አገኙ፡፡ ነገር ግን ወደ አምባው መግቢያ በር ባለማግኘታቸው ወደፈጣሪያቸው ጸሎት ማድረሱን ቀጠሉ በዚህ ጊዜ በቀራንዮ አደባባይ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሆኖ ሥጋውን ሲቆርስ ደሙን ሲያፈስ በጽዋዕ ብርሃን ተቀበሎ ደሙን ቤተ ክርስቲያን በሚሠራበት ቦታ ሁሉ የረጨው ሊቀ መላእክት ቅዱስ ዑራኤል  ዐፄ ዘርዓ ያዕቆብንና ሠራዊታቸውን መስቀሉን ይዘው በሚጓዙበት ሁሉ እየባረከና እየረዳቸው ግሸን አምባ ተራራን ሦስት ጊዜ ዞረው ጸሎት ካደረጉ በኋላ አዳል ሜዳ በሚባለው ቦታ ‹‹በዚህ በኩል መስቀሉን ይዘህ ውጣ›› ብሎ ገለጸላቸው፡፡ ዐፄ ዘርዓ ያዕቆብም በጣም ተደስተው በአዳል ሜዳ በኩል ባለው ገደል እየተንጠላጠሉ መስቀሉን ወደ ተራራው አውጥተው መስከረም 21 ቀን 1449 ዓ.ም  የእግዚአብሔር አብ ቤተመቅደስን በጥሩ ሁኔታ አሳንጸው መስቀሉንና በርካታ ንዋያተ ቅዱሳትን በብልሃትና በጥንቃቄ እንዲቀመጥ አደረጉ የእመቤታችንን ቤተመቅደስም ንግሥት እሌኒ አሳንጹ።

 

ከዘመናት በኋላ በ1940 ዓ.ም አካባቢ የተራራው እግረ መስቀሉ  በሆነው እና ደላንታ ሜዳ በተበለው ቦታ ላይ ብጹዕ አቡነ ሚካኤል የቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን አሰሩ፡፡ ኋላም ቀድሞ የነገሥታት ልጆች ይማሩበት በነበረው ቦታ ላይ ከአዳል ሜዳ ከፍ ብሎ በሚገኘው ቦታ ላይ በ1979 ዓ.ም የቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ተሠራ፡፡

 

በስተምሥራቅ አቅጣጫ በቅዱስ ዑራኤል መሪነት መስቀሉ የገባበትና ቀድሞ ያረፈበት አዳል ሜዳ ከግሸን ተራራ መስቀለኛ አቀማመጥ አንፃር ሲታይ ሰፊና ማራኪ የመሬት አቀማመጥ አለው፡፡ ነገር ግን ከ500 ዓመታት በላይ በቦታው ቤተ ክርስቲያን ሳይሠራ ቆይቷል፡፡ ‹‹ጊዜ ሲደርስ አምባ ይፈርስ›› እንዲሉ አበው፤ አዳል ሜዳ ቅዱስ ዑራኤል መስቀሉ ወደ ተራራው እንዲገባ የመራበት፤ መስቀሉ ያረፈበት ቦታ በቅዱስ ዑራኤል ስም ቤተ ክርስቲያኑ እንዲታነጽ መስከረም 1994 ዓ.ም በአንድ ምእመን ሊሠራ ታስቦ የደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሆኑት በአቡነ አትናቴዎስ ተባርኮ ሥራው ሊጀመር ቻለ፡፡ ሆኖም ግን የሕንፃ ሥራው ቢጀመርም በተለያዩ ምክንያቶች ሥራው ሊቀጠል አልቻለም፡፡ ለዓመታትም ባለበት ሁኔታ ቆመ፡፡  ኋላም በ2004 ዓ.ም ስማቸው እንዲጠቀስ ባልፈለጉ አንድ ምእመን የቅ.ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን ተሠርቶ ለአገልግሎት ዝግጁ ሆነ፡፡

 

7

ቤተ ክርስቲያኑን በገንዘባቸው ያሠሩት ምእመን  ስለ ቤተ ክርስቲያኑ አጀማመርና የሥራውን መፋጠን ሲገልጹ “የቤተ ክርስቲያኑ ሥራ ተጀምሮ በመቆሙ ሁሌ ያሳስበኝ ነበር፡፡ ግሸን በመጣሁ ቁጥር ጅምሩን ቤተ ክርስቲያን ተሳልሜ ጸሎት አድርጌ እመለሳለሁ፡፡ ለምን እኛ አንሠራውም የሚል ሀሳብ መጣልኝ ጉዳዩንም ከጓደኞቼ ጋር ተወያየን፡፡ ከሰበካ ጉባኤው አባላት ጋር ውይይቶች አድርገን  ፈቃዳቸውን ገለጹልን፡፡  በዚህ መሰረት ኅዳር 17 ቀን 2004 ዓ.ም ቤተ ክርስቲያኑን እንድንሠራ ተስማማን፡፡ ተፈራረምን፡፡ ”በማለት ገልጸው በአጭር ጊዜ ተሠርቶ ማለቁን ሲያብራሩ አሰሪው  ‹‹ይገርመኛል የግሸን ተራራ መንገድ ለትራንስፖርት አይመችም ያውም በክረምት ግን በስድስት ወር መጠናቀቁ  ሊቀ መልአኩ የሠራው መሆኑን ነው የሚረዳኝ›› ለወጣቶች ምን ምክር አለዎት? ብለን ላቀረብንላቸው ጥያቄ ‹‹ቤተ ክርስቲያንን የሚሠራው እግዚአብሔር ነው፡፡ ትልቁ ነገር መልካም ልቦና መያዝና  የእግዚአብሔርን ፈቃድ መጠየቅ ነው፡፡ ›› በማለት ገልጸውልናል፡፡

 

ሕንፃውን ለማሠራት በአሰሪው ምእመን የተወከሉት መምሬ እሸቱ ስለ ቤተ ክርስቲያኑ ሕንፃ ሥራ መፋጠን ሲገልጹ ኅዳር 17 ቀን 2004ዓ.ም፡፡ ቤተ ክርስቲያኑን ለመሥራት ቢወሰንም ሥራው የተጀመረው ታኅሣሥ 5 ቀን 2004 ዓ.ም ነው ፡፡  በስድስት ወር ጊዜ ውስጥ ግን ከዚህ  መድረሱ የመልአኩ ርዳታ ታክሎበት ነው፡፡ እኔ ያደኩበት ያገለገልኩበት ቦታ ነው ፡፡በተለይ ይህንን ቤተ ክርስቲያን ተወክዬ ማሠራቴ በጣም አስደስቶኛል፡፡ የቦታውን ክብርና ታሪክ አውቃለሁና፡፡

 

የደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ አባ ገ/ሥላሴ የቅዱስ ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን መሥራትን አስመልክተው ሲገልጹልን ‹‹የቅዱስ ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን በዚህ ቦታ (አዳል ሜዳ) መሥራት የግሸን አምባን ሃይማኖታዊና ታሪካዊነት ማጉላት ነው፡፡ እያንዳንዱ ክንፍ ስያሜ አለው ይህ ክንፍ አዳልሜዳ ይባላል፡፡  የቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ያለበት ቦታ ደላንታ ሜዳ ፣ዋናው በር፣ በግራ ክንፍ ያለው ቦታ መሳቢያ ወይም ጋሻውድም ይባላሉ፡፡ ዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ መስቀሉን በኢትጵያ ምድር ለሦስት ዓመታት ይዘው ከዞሩ በኋላ፤ ከመስቀሉ ጋር ከፍተኛ ግንኙነት ያለው ቅዱስ ዑራኤል  ንጉሡ የግሸን አምባ ተራራ መግቢያ በቸገራቸው ሰዓት ‹‹በዚህ በኩል መስቀሉን ይዘህ ግባ›› በማለት አዳል ሜዳ በተባለው በኩል እንዲገቡ አድርጓቸዋል፡፡ በዚህ ምክንያት የቅዱስ ዑራኤልን ቤተ ክርስቲያን በግሸን ተራራ ላይ መሥራት፣ ማሠራት፣ መተባበር መታደል ነው፡፡ ባለታሪክ መሆን ነው፡፡ የሃይማኖቱ ዋጋ ተካፋይም ነው፡፡ ” በማለት ገልጸዋል።

 

የቅዱስ ዑራኤልን ቤተ ክርስቲያን ህንጻ ሥራ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠቱን የሚናፍቁት የግሸን ደብረ ከርቤ ማርያም አስተዳደሪ ሊቀ ሊቃውንት ቆሞስ አባ  ተክለማርቆስ ከደስታቸው ብዛት የተነሣ ንግግራቸውን ከምርቃት ይጀምራሉ፡፡ ‹‹መልአኩ አይለያችሁ ለሥጋም ለነብስም ዋስ ጠበቃ ይሁናችሁ፡፡ ቦታውን እንዳሰባችሁት እሱ ያሰበላችሁ፡፡” ብለው ንግግራቸውን ይጀምራሉ ‹‹አሁን ቤተልሔሙን ከሠራን አገልግሎቱን መቀጠል እንችላለን፡፡ እስካሁንም የመንገዱ ሁኔታ ባለመመቸቱ እንጂ ይጠናቀቅ ነበር፡፡ ተመስገን ነው ፈቃዱ ከሆነ ጥር 22 ቀን 2005 ዓም.ቤተ ክርስቲያኑ ተመርቆ አገልግሎት መስጠት ይጀምራል፡፡” በማለት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል ፡፡

 

እኛም ጥር 22 ቀን 2005ዓ.ም በግሸን አምባ ተራራ የቀድሞ መግቢያ(አዳልሜዳ) ላይ የተሠራውን የቅ.ዑራኤል ቤተ ክርስቲያን ምረቃ ላይ እንድንገናኝ እግዚአብሔር ይርዳን እንላለን፡፡

2 (2)

የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የድኅረ ምረቃ መርሐ ግብር ጀመረ

ጥቅምት 29 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


2 (2)ቅዳሜ ጥቅምት 24 ቀን 2005 ዓ.ም በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የመሰብሰቢያ አዳራሽ፤ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የኮሌጁ የቦርድ አባላት፣ የአስተዳደር ሠራተኞች፣ መምህራንና ተማሪዎች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በጸሎት በተከፈተው ጉባኤ፥ ኮሌጁ የሁለተኛ ዲግሪ መርሐ ግብር መጀመሩ በይፋ ተበስሯል፡፡

 

የእንኳን ደህና መጣችሁና የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ የቅድሰት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሓላፊና፥ የቅዱስ5 ሲኖዶስ አባል፤ ኮሌጁ፥ ከጊዜ ወደ ጊዜ በእግዚአብሔር ፈቃድ እያደገ ከፍተኛ የነገረ መለኮት ኮሌጅ ለመሆን መብቃቱን አውስተው፥በተለይ አፄ ኀ/ሥላሴ ለኮሌጁ ያበረከቱትን አስተዋጽኦ ሲናገሩ፡- “አሁን ኮሌጁ የሚገኙበትን ቦታ፥ የቤተ ክርስቲያንና የሀገሪቱ አባት የነበሩት ግርማዊ ቀዳማዊ አፄ ኀይለ ሥላሴ ለመንፈሳዊ ትምህርት ከነበራቸው ቅን አስተሳሰብ በመነጨ ቦታውን ‘የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት’ ተብሎ እንዲሰየምና አገልግሎት እንዲሰጥ አበርክተዋል፡፡ ግርማዊነታቸው ለቤተ ክርስቲያኒቱ በሠሯቸው በጎ ሥራቸው ሲታሰቡ ይኖራሉ፡፡ ”በማለት ገልጸው፥ኮሌጁ የመክፈቻ ንግግራቸውን ያደረጉት ከጥቅምት 24 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ በሲስተማቲክ ቲዎሎጂ የሁለተኛ ዲግሪ መርሐ ግብር ለመጀመር እንደተቻለ አስታውቀዋል፡፡

 

ከብፁዕነታቸው የመክፈቻ ንግግር ተከትሎ ስለኮሌጁ ታሪካዊ ዳሰሳ ያቀረቡት ዶ/ር አባ ኀይለ ማርያም መለሰ የኮሌጁ 4 (2)ምክትል ዋና ዲ/ን፡- “የትምህርት መድረክ የጥበብ መደብር ነው፡፡ ለአያሌ ዘመናት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ብቸኛዋ የእውቀት ቀንዲል አብሪ ሆና ቆይታለች፡፡ ይህ የተቀደሰ ተልዕኮዋም እየሰፋና እያዳበረ ሄዶ ለዛሬ በቅተናል፡፡ ለዚህም አንዱ ዓይነተኛ መሣሪያ ይህ ከፍተኛ የትምህርት ማእከል ነው፡፡ በእግዚአብሔር ስም የተመሠረተ እውቀት መንፈሳዊ እየተስፋፋ በሄደ ቁጥር፥ የቤተ ክርስቲያናችን ክብር፣ የሃይማኖታችን ጽናት፣ የሀገራችን ፍቅር፣ ሰላምና አንድነት ይጠበቃል ይጠነክራል ይልቁንም ትውልዱ እግዚአብሔርን የሚፈራ ግብረ ገብነት ያለው ይሆናል፡፡

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከአንድ ሺህ አምስት መቶ ዘመን በላይ በሀገራችን በኢትዮጵያ የትምህርት ማዕከል ሆኖ ቆይታለች ይኸንኑ ለረጅም ዘመን በበላይነትና በብቸኝነት የቆየ መንፈሳዊ ትምህርት በዘመናዊው የማስተማር ስልት (ዘይቤ)  ማከናወን ይቻል ዘንድ በ1934 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ግርማዊ ቀዳማዊ ዓፄ ኃይለ ሥላሴ፥ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅን ‘የካህናት ፎረም’ በሚል ስያሜ በቤተ መንግሥታቸው መሠረቱት፣” በማለት ስለ ታሪካዊ አመሠራረቱ ካወሱ በኋላ በ1935 ዓ.ም. የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የተመሠረተበት የገነት ልዑል ቤተ መንግሥት አሁን ወዳለበት ቦታ ተዛወሮ በዚሁ ዘመን ግርማዊነታቸው የቅድስት ሥላሴን መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ሕንፃ የመሠረት ድንጊያ እንዳስቀመጡ ገልጸዋል፡፡

 

በስተመጨረሻም በዛሬው እለት ለተሰባሰብንበት የድኅረ ምረቃ መርሐ ግብር ኮሌጁ ለዚህ መብቃቱ ለመላው የቤተ ክርስቲያን አማኞችና2 (1) ወዳጆቿ ታላቅ የምሥራችና ደስታ ነው፡፡ ይህን መርሐ ግብር ለመጀመር ከፍተኛ አባታዊ አመራር የሰጡንን የኮሌጃችንን ኃላፊ ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስን፣ እንዲሁም የአመራር ቦርዱን፣ መምህራንና የቢሮ ሠራተኞችን ለዚህ ስኬት በመሥራታቸው ልባዊ ምስጋናዬን አቀርባለሁ” በማለት ንግግራቸውን አጠናቀዋል፡፡

 

ከዶክተር አባ ኀይለማርያም ንግግር ቀጥሎ በመምህር ፍስሐጽዮን ደሞዝ የኮሌጁ ምክትል አካዳሚክ ዲን ስለኮሌጁ አካዳሚክ እድገትና ስለድህረ ምረቃ መርሐ ግብር አጀማማር ሪፖርት ቀርቧል፡፡

 

6‘‘ኮሌጁ ከተከፈተ ጊዜ ጀምሮ ለረጅም ዓመታት ደቀመዛሙርትን ያሰለጥን የነበረው በዲፕሎማ እና በዲግሪ መርሐ ግብሮች ሲሆን ከ2002 ዓ.ም ጀምሮ ግን በልሳነ ግእዝ ዲፕሎማ፣ በርቀት ሰርተፍኬት፣ በድህረ ምረቃ ዲፕሎማ(PGD) እና በዘንድሮው የትምህርት ዘመን ደግሞ ለመጀመሪያ ጊዜ የድህረ ምረቃ የሁለተኛ ዲግሪ መርሐ ግብሮችን ሊጀምር ችሏል፡፡ ከነዚህ ፕግራሞች በተጨማሪ በቀጣይ በርቀት ትምህርት ዲፕሎማ መርሐ ግብርን ለማስጀመር አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት አጠናቅቋል፡፡’’በማለት የተናገሩት  ምክትል አካዳሚክ ዲኑ የሁለተኛ ዲግሪ መርሐ ግብር ለመጀመር ያስፈለገበትን ምክንያት ሲያብራሩ አራት ነጥቦችን ጠቅሰዋል፡፡ እነርሱም

 

1ኛ. የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በ21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ዶግማዋን፣ ቀኖናዋን፣ ሥርአቷን፣ ትውፊቷን እና ባሕሏን እንዲሁም አንድነቷን ጠብቃ ወደፊት እንድትራመድ የሚያስችላት ትውልድ ተሻጋሪ የሆነ ከፍተኛ የጥናትና ምርምር ተቋም እንዲኖራት ለማስቻል፣

 

2ኛ ቤተ ክርስቲያናችን ከፊቷ ከተጋረጡባት ተግዳሮቶች ማለትም ከዘመናዊነትና ከሉላዊነት (globalization) ራሷን የምትከላከልበት በነገረ መለኮት ትምህርት የበሰሉ መምህራንና ደቀ መዛሙርትን ለማፍራት፡

 

3ኛ. ቤተ ክርስቲያናችን በሀገር ውስጥ እና ከሀገር ውጪ ካሉዋት ተከታዮች አንፃር ሲታይ ያልዋት ከፍተኛ የነገረ መለኮት ተቋማት እጅግ በጣም አነስተኛ ስለሆኑ በዚህ በድኅረ ምረቃ ፕሮግራሙ በቂ የሰው ኀይልን እና ምሁራንን በማፍራት እንደሌሎቹ አኅት አብያተ ክርስቲያናት ተጨማሪ የነገረ መለኮት ኮሌጆች ለመክፈት የሚያስችላትን አዲስ ዕድል ስለሚፈጥር፣

 

4ኛ. የድኅረ ምረቃ ፕሮግራሙ ከፍተኛ ጥናት እና ምርምር የሚደረግበት ስለሆነ ቤተ ክርስቲያናችን በሀገር ውስጥ እና በውጪ ሀገር አንድነቷ ተጠብቆ እንዲቆይ የሚያስችሏትን የመጻሕፍት ትርጉም ሥራዎች፣ የወንጌል አገልግሎትን ለማስፋፋት የምትከተላቸውን ስልቶችና ዘዴዎችን እንዲሁም በተለያዩ የቤተ ክርስቲያናችን ጉዳዮች የሚያጠነጥኑ ጥናቶችን እና ምርምሮችን በማድረግ ችግር ፈቺ እና የመፍትሔ አቅጣጫዎችን ጠቋሚ የሆኑ መረጃዎችን ለማግኘት ይህ ፕሮግራም እንደ ምንጭ ሆኖ ያገለግላል፡፡ ’’ በማለት ተናግረዋል፡፡

 

ከምክትል አካዳሚክ ዲኑ ሪፖርት ለመረዳት እንደተቻለው ኮሌጁ በ2005 ዓ.ም. የትምህርት ዘመን ለመጀመሪያ ጊዜ በመደበኛው መርሐ 4 (1)ግብር 33 ደቀ መዛሙርትን ተቀብሎ የመማር ማስተማሩን ሂደት ጀምሯል፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ማጠናቀቂያ ላይ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የሁለተኛ ዲግሪ የማስትሬት መርሐ ግብሩ  መጀመሩን በይፋ አብስረዋል፡፡

pop twadros election

የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን 118ኛውን ፓትርያርክ መረጠች

ጥቅምት 26 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለ40 ዓመታት ቤተ ክርስቲያኗን ሲመሩ የነበሩትንና በቅርቡ ያረፉትን ፓትርያርክ ብፁዕ አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊን ለመተካት 118ኛውን ፓትርያርክ እሑድ ጥቅምት 25 ቀን 2005 ዓ.ም. በታላቅ ሥነ ሥርዓት መረጠች፡፡

pop twadros electionበካይሮ አባሲያ ቅዱስ ማርቆስ ካቴድራል በተደረገው የእጣ አወጣጥ ሥነ ሥርዓት በእጩነት ከቀረቡት 3ቱ አባቶች መካከል አንዱን በፓትርያርክነት ለመሾም ዓይኑን በጨርቅ የተሸፈነ ሕፃን እጣውን እንዲያወጣ በማድረግ ብፁዕ አቡነ ታዋድሮስ / ቴዎድሮስ/ የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ሆነው ተመርጠዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ታዋድሮስ በ1952 እ.ኤ.አ የተወለዱ ሲሆን በፋርማሲ ሳይንስ ከአሌክሳንደሪያ ዩኒቨርስቲ ተመርቀዋል፡፡ከ1997 pop twadrosእ.ኤ.አ ጀምሮ በጵጵስና ተሹመው የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን በማገልገል ላይ ነበሩ፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ አምስት ጳጳሳትን ያቀፈ ልዑክ ወደ ግብጽ በመላክ በምርጫው ላይ ተሳትፈው መመለሳቸው ይታወሳል፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በጎቿን ይዛ እንድትዘልቅ …

ጥቅምት 26 ቀን 2005 ዓ.ም.


በየዓመቱ በጥምቀት ወር በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የአስተዳደርና ዘርፈ ብዙ አገልግሎት ላይ የሚመክረው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ለሠላሳ አንደኛ ጊዜ ተካሂዷል፡፡ በዚህ ጉባኤ ላይ የእናት ቤተ ክርስቲያናቸውን የአገልግሎት ጥሪ የተቀበሉ ምሁራን ልጆቿ፤ በልዩ ልዩ ርእሰ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ ጥናት ጽሑፎቻቸውን አቅርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ በእንደዚህ ዓይነቱ ታላቅ ጉባኤ ላይ፤ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሁለንታዊ አገልግሎት መቃናት የሚበጁ፣ በየሙያ ዘርፉ ዕውቀትና ልምድ ባካበቱ ምሁራን ልጆቿ የሚቀርቡ የጥናት ጽሑፎችና የሚካሄዱ ውይይቶች፤ እናት ቤተ ክርስቲያን ትውልዱን ይዛ ዘመኑን እየዋጀች ጸንታ እንድትቀጥል በማድረግ ረገድ ጠቀሜታቸው የጎላ ነው፡፡

 

በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የአገልግሎት ዘርፎች የተቀላጠፈና ዘመናዊ የአስተዳደር መዋቅርና አሠራር እንዲኖር ማድረግ ወቅቱም ሆነ ትውልዱ የሚጠይቀው ጉዳይ ነው፡፡ በዕቅድ ላይ የተመሠረተ በሪፖርትና ትክክለኛ ክትትል ባልተለየው ግምገማ የተደገፈ፣ ሓላፊነትና ተጠያቂነት ያለበት ማእከላዊ የፋይናንስ አስተዳ ደር ሥርዐት እንዲሰፍን ተጨባጭ ጥረት ያስፈልጋል፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቷ መንፈሳዊ ፍርድ ቤቷ ተጠናክሮ አስተዳደሯ፣ ሥርዐተ ከህነቷም ሆነ ሁለንተናዊ አገልግሎቷን የሚመለከቱ እንዲሁም የምእመናን መንፈሳዊ ጉዳ ዮች የሚዳኙበት አስተምህሮና ቀኖናዋን የጠበቀ መንፈሳዊ የፍትሕ ሥርዓት ተግባራዊ እንዲሆን ማድረግ ችላ የሚባልበት ወቅት አይደለም፡፡

 

ከሐዋርያዊ ተልእኮዋ ባሻገር በማኅበራዊ አገልግሎቷም የበለጠ እንድትሠራ፤ በልማት ሥራ እንድትበለጽግ፣ ገዳማቷና አድባራቷ በገቢ ራሳቸውን ችለው ከልመና እንዲላቀቁ በማድረግ ረገድ ከፍተኛ ሥራ ይጠበቅባታል፡፡ በእነዚህ ሁሉ መስኮች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ምሁራን ልጆቿን በማሳተፍ በጥናትና ምርምር የተደገፈ ውጤታማ ሥራ ለመሥራት ቀዳሚ ትኩረት መስጠት እንዲሁም ሁኔታዎችን ማመቻቸትና የበለጠ ጥረት ማድረግ አለባት፡፡

 

አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ያለው ታላቅ መድረክ፤ በተራዘመ ሪፖርትና በተደጋገመ መልእክት የሚባክነው ጊዜ፤ በዓመት አንድ ጊዜ ከሚገኘው ጉባኤ ለቤተ ክርስቲያን የሚበጅ አሳብ፣ ዕቅድና መፍትሔ የሚቀርብበትን ምቹ ሁኔታ በማሳጣት ያለጥቅም እንዲያልፍ ያደርጋል፡፡ ለተሻለ አሠራርና ለበለጠ ውጤት የሚያበቃ የውይይት መድረክ የሚሆንበትን ዕድል ይነፍጋል፡፡

 

ስለዚህ እንዲህ ዓይነቶቹን ክፍተቶች በመገንዘብ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሁለን ተናዊ አገልግሎት የሚበጅ የጥናት ጽሑ ፎች እንዲቀርቡ ሐሳብ በመስጠት፣ ዕቅድ በማውጣት፣ ጊዜ፣ በጀትና የሰው ኀይል መድቦ ውይይቱ እንዲካሄድ የተደረገው ጥረትና የተከናወነው ሥራ የሚመሰገን ሲሆን ወደፊትም በተሻለ ሁኔታ ሊቀጥል የሚገባው ተግባር ነው፡፡

 

የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ጥሪ ተቀብለው እውቀታቸውንና ሙያዊ ልምዳቸውን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በሚበጅ ተግባር ላይ ለማበርከት በቀናነት የተሳተፉት ምሁራን ልጆቿ የሚመሰገኑ ናቸው፡፡ አገልግሎታቸው ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልእኮ መቃናት፣ በዘመናዊ አሠራር በተደራጀ አስተዳደራዊ መዋቅር ዘርፈ ብዙ አገልግሎቷ የተሳካ አፈጻጸም እንዲኖረውና በልማት እንድትበለጽግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረክታል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ አገልግሎት በልዩ ልዩ የሥራ መስኮችና ቦታዎች የተሰማሩት ምሁራን ልጆቿ በየተሰጣቸው ጸጋና ሞያ ለቤተ ክርስቲያን የሚጠበቅባቸውን አገልግሎት እንዲያበረክቱ በማነሣሣት ረገድ በአርአያነት የሚጠቀስ ነው፡፡

 

በየደረጃው ያሉት የቤተ ክህነቱ መዋቅርና አካላት ይህንኑ በጎ ልምድ መነሻ በማድረግ፤ በተለያየ ሙያና የሥራ መስክ የተሰማሩ ምሁራን በቤተ ክርስቲያን ልጅነታቸው ድርሻቸውን እንዲያበረክቱ በራቸውን ክፍት ማድረግና የአገልግሎት መድረኮችን ማመቻቸት እንደሚጠበቅባቸው ያመላክታል፡፡

 

በሠላሳ አንደኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ላይ ከቀረቡት ጽሑፎች መካከል፤ ለምሳሌ “የዘመናችንን ትወልድ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ለማብቃት የአባቶች ሚና” በሚል ርእስ የቀረበው ጽሑፍም ከላይ ያነሣና ቸውን ነጥቦች በአጽንዖት የጠቆመ ነው፡፡

 

በጥናት ወረቀቱ እንደተጠቀሰው፤ የሕዝብ ብዛት እየጨመረ በመምጣቱ ምክንያት ጎልቶ አይታይ ይሆናል እንጂ በየጊዜው ሃይማኖታቸውን የሚተው፣ ከቤተ ክርስቲያናቸው የሚኮበልሉ ምእመናን ቁጥር ቀላል አይደለም፡፡ ምእመናንን ወደ ውጪ የሚገፉ በርካታ ውስጣዊና ውጫዊ ምክንያቶች አሉ፡፡ ከእነዚህም ምክንያቶች አንዱና ዋነኛው ከቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ጋር የሚያያዝ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎቶች ይበልጥ እየተሻሻሉ ዘመኑን መዋጀት ካልቻሉ ውጤቱ ያማረ አይሆንም፡፡ ለዚህም ነው የዛሬውን ትውልድ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ብቁ እንዲሆን ማድረግ ወሳኝ ጉዳይ የሚሆነው በማለት የቀረበው ሐሳብ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ነው፡፡

 

ምናልባትም በታላላቅ ከተሞች ባሉ ገዳማትና አድባራት የሚታየው እንቅስቃሴ፤ በወርና በዓመት የንግሥ ወይም ዐበይት በዓላት የሚታየው የሕዝበ ክርስቲያኑ ብዛትና ድምቀት በየገጠሩና በየበረሐው ያለውን አገልግሎት እንቅስቃሴና የምእመናኑን መጠን የሚያሳይ ነው የሚል የተሳሳተ ግምት ካለ፤ ገሐድ እውነቱ ከተሳሳተው ግምት የተለየ መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

 

ስለዚህ ትውልዱን በቤተ ክርስቲያን እቅፍ ሰብስቦ ለአገልግሎት በማብቃት የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ አገልግሎት ዘመኑን በዋጀ ውጤታማ አሠራር በተሳካ ሁኔታ ማፋጠን የወቅቱ ጥያቄ ነው፡፡ አሁን ባለው ዘመንና ትውልድ ደግሞ ሉላዊነትን (Globalization) መሠረትና ጉልበት ያደረገ ሥልጣኔ የተስፋፋበት፣ ዘመናዊነት የነገሠበት እንደመሆኑ፤ በዓለማችን የሚከሠቱ ተጨባጭ ሁኔታዎች በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ አሉታዊም ሆነ አዎንታዊ ተጽዕኖ አቸው እያየለ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሕልውናና አገልግሎት ፈተናዎች እየሆኑ ይታያል፡፡

 

ከዘመኑ የኑሮ ሁኔታ፣ የሥልጣኔ ውጤቶች፣ በተዛባ የዘመናዊነት ግንዛቤ የሚከሠቱት ዓለም አቀፋዊ ተጽዕኖዎች በተለይ በመንፈሳዊ ሕይወቱ የሚያሳድሩበትን ጫና እንዲቋቋም አድርጎ ለጥያቄዎቹ ምላሽ በመስጠት ትውልዱን ይዞ ለመቀጠል ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አፋጣኝ መፍትሔ ልትሰጠው የሚገባ ተግባር ነው፡፡

 

ስለዚህ በየአጥቢያው የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን ማስፋፋት፣ ጉባዔያትን ማጠናከር፤ ለሰንበት ትምህርት ቤቶች ልዩ ትኩረት ሰጥቶ በቅርበት ዕለት ዕለት መከታተል፣ መምህራነ ወንጌል መመደብ፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማሟላት፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን በማጠናከርና በማስፋፋት አገልግሎታቸውም በበለጠ ጥረት የተሻለ ውጤት እንዲኖረው በማድረግ ረገድ ከፍተኛ ሥራ ይጠበቃል፡፡

 

ከፍተኛ የመንፈሳዊ ትምህርት ተቋማቱን በተሟላ አደረጃጀትና ዘመናዊ አሠራር እያጠናከሩ ማስፋፋት እውነተኛ የቤተ ክርስቲያን ልጆች በቀና ዓላማ ገብተው በቂ ዕውቀት ቀስመው ለአገልግሎት እንዲዘጋጁ ያስችላቸዋል፡፡ ሌሎችም የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መንገዶችን የቴክኖሎጂውን እድገትና ዕድል በመጠቀም፤ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ በመላው ዓለም በየቦታው ላይ ለምእመናን፤ በመገናኛ ብዙኃን ቃለ እግዚአብሔርን ማድረስ የግድ ይላል፡፡

 

አብነት ትምህርት ቤቶቻችን በብዙ ችግሮች ተተብትበው መምህራኑም ሆኑ ደቀ መዛሙርቱ ፈተና ላይ ወድቀዋል፡፡ የትምህርት አሰጣጥ ዘዴው ጊዜን፣ ቁሳዊ ሃብትን፣ ወቅትንና ሌሎችም አካባቢያዊ ሁኔታዎችን ባገናዘበ ሁኔታ ተመቻችቶ ባለመካሄዱ በቀጣይነቱ ላይ የተጋረጠ ትልቅ ፈተና ነው፡፡ ችግሮቹን አዝሎ ያንዣበበው አደጋ ከቀጠለ የካህናትና ሊቃውንት አገልጋዮቿ ምንጭ እየተዳከመ የነገይቱ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ስኬትም አጠያያቂ መሆኑን ከወዲሁ ማሰብ፤ አፋጣኝ መፍትሔ መፈለግና በተግባር ማረጋገጥ አስፈላጊ ነው፡፡ ሊቃውንቱ እንዲያስተምሩ፣ የተካበተ ዕውቀታቸው ለምእመናን እንዲደርስ መርሐ ግብር ማዘጋጀት፣ መድረኮችን ማመቻቸትና እንዲሳተፉ ማድረግ ይገባል፡፡ ከዚህም በላይ ሰፊ የዕውቀት ሀብታቸው፣ ከመንፈሳዊው አገልግሎትና ሕይወታቸው ልምድ ጋር ለትውልድ እንዲተላለፍ ምእመናን እንዲጠቀሙበት ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንዲጽፉ ማበረታታት፣ የሚያስፈልጋቸውን ማገዝ ማሳሰብ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡

 

የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባቶችና አገልጋዮች ትውልዱን ከማስተማር ጎን ለጎን የዕለት ተዕለት ክትትልና መንፈሳዊ ጥበቃ ማድረግ እንዳለባቸው ዋነኛ የአባትነት ሓላፊነታቸው እንደሆነ የታወቀ ነው፡፡ ከዚሁ ጋር በሕይወታቸው መልካም አርአያ በመሆን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መትጋትና ሃይማኖታዊ ሓላፊነታቸውን በሚገባ መወጣት አለባቸው፡፡

 

በአጠቃላይ በጎቹን በቃለ እግዚአብሔርና በመንፈሳዊ ሕይወት ጠብቆ በእናት ቤተ ክርስቲያን እቅፍ እንዲዘልቅ፤ በቀና መንፈስ በአገልግሎት እንዲሳተፍ ማስቻል፣ በፍቅርና በመልካም የአባትነት አርአያ መቅረብ፣ መከታተል ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ቀዳሚ ሥራ ነው እንላለን፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት ቁጥር 4 2005 ዓ.ም.

በማኅበረ ቅዱሳን የአርባ ምንጭ ማእከል 14ኛውን ጠቅላላ ጉባኤ እየተካሄደ ነው

ጥቅምት 24 ቀን 2005 ዓ.ም.

ከአርባ ምንጭ ማዕከል


በማኅበረ ቅዱሳን የአርባ ምንጭ ማእከል ከጥቅምት 23-25ቀን 2005 ዓ.ም 14ኛውን ጠቅላላ ጉባኤ በመካሔድ ላይ ነው ፡፡ በመክፈቻ መርሐ ግብሩ ላይ ከሀገረ ስብከት የመምሪያ ሓላፊዎች፣ በአርባ ምንጭ ከተማ የሚገኙ የአድባራት አስተዳዳሪዎች እና ሰበካ ጉባኤያት፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ተወካዮች ፤  የ16 ወረዳ ማእከላት እና 3 ግንኙነት ጣቢያዎች ፤ የ10 ግቢ ጉባኤያት ተወካዮች እና ጥሪ የተደረገላቸው ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል፡፡

 

ለሁለት ቀናት በሚቆየው ጉባኤ የማእከሉ የ2004 የሥራ ክንውን ሪፖርትና የ2005 ዕቅድ ቀርቦ ውይይት የሚያካሂድ ሲሆን በተጨማሪም በተለያዩ አጀንዳዎች ዙሪያ ውይይት ያደርጋል፡፡

 

  • በተለይም ትኩረት የሚደረግባቸው አጀንዳዎች
  1. የአራት ዓመቱ ስትራቴጂክ እቅድ አፈፃፀም
  2. የወረዳ ማእከላት እንቅስቃሴ የሚያሳይ የዳሰሳ ጥናት
  3. የአብነት ትምህርት ቤቶችና የአብያተ ክርስትያናት የልማት እንቅስቃሴዎችን ማሳየት
  4. ግቢ ጉባኤያትን ለሐዋርያዊ አገልግሎት ማብቃት

በሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት በማድረግ ውሳኔዎችን ያሳልፋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የማእከሉ ሰብሳቢ አቶ ገናነው ፍሰሐ ገልጸዋል፡፡