dsc03541

የአሰቦት ገዳም የመንገድ ችግር በመቀረፍ ላይ ነው

ኅዳር 20 ቀን 2005 ዓ.ም.
በእንዳለ ደምስስ

•    በሁለት በጎ አድራጊ ወጣቶች የ6 ኪሎ ሜትር የተራራው አስቸጋሪ መንገድ ተሠራ
•    የ12 ኪሎ ሜትሩ መንገድ በመሠራት ላይ ነው

dsc03541የአሰቦት ደብረ ወገግ ቅድሥት ሥላሴና አቡነ ሳሙኤል ገዳም 6 ኪሎ ሜትር የተራራው መውጫ መንገድ በሁለት በጎ አድራጊ ወጣቶች ሙሉ ወጪውን በመሸፈን የጥርጊያ መንገዱን ሥራ ከመስከረም 7 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ  በ17 ቀናት ውስጥ በመሥራት ተጠናቀቀ፡፡

የገዳሙ አበምኔት አባ ተክለ ማርያም ተክለ ፃድቅ ስለ መንገድ ሥራው ሲገልጹ “እግዚአብሔር አነሣሥቷቸው ይህ ቅዱስ ገዳም ያለበትን የመንገድ ችግር ተገንዝበው ሙሉ ወጪውን በመሸፈንና መንገዱ ተሠርቶ እስኪጠናቀቅ ድረስ እዚሁ ከእኛው ጋር በመሆን ሥራውን እየተቆጣጠሩ በአጭር ጊዜ ውስጥ ማጠናቀቅ ተችሏል፡፡ የመንገዱ መሠራት ገዳሙን ከእሳት ቃጠሎ፤ በተለይም የደን ጭፍጨፋ ከሚያካሂዱ አካላትና ከተለያዩ አደጋዎች ይታደገዋል፡፡ ምእመናንም ከዚህ ቅዱስ ሥፍራ በመገኘት በረከት እንዲቀበሉ ያስችላቸዋል፡፡ ለኛ ለገዳማውያንም መውጣት መውረዱን ያቀልልናል፡፡ ሁለቱ ወጣቶች ያከናወኑት በጎ ተግባር ሌሎችም አርአያነታቸውን ሊከተሉ ይገባል  ” ብለዋል፡፡

 

ቴዎድሮስ ሰሎሞን ይባላል፡፡ የ”ዴታና ቢዝነስ ሓላፊነቱ የተወሰነ ግል ማኅበር” ባለቤት ነው፡፡ የ6 ኪሎ ሜትር የተራራውን ጥርጊያ መንገድ ከጓደኛው ጋር በመሆን  ሙሉ ወጪውን በመሸፈን ለመሥራት በቅቷል፡፡ ምን እንዳነሣሣው ጠይቀነው ሲመልስ “አሰቦት ገዳም ላለፉት 10 ዓመታት በዓመታዊ ንግሥ በዓል ላይ በረከት ለማግኘት ተመላልሻለሁ፡፡ ዋነኛ ችግር ነው ብዬ የተመለከትኩትም ምእመናን ተራራውን ለመውጣት የሚያደርጉትን አድካሚ ጉዞ ነበር፡፡ አረጋውያን መውጣት ተስኗቸው በየመንገዱ እያረፉ ሲጨነቁና ሲጠበቡ እመለከታለሁ፡፡ ይህንን መንገድ መች ነው የምሠራው እያልኩ ሳስብ ቆይቻለሁ፡፡ አሰበ ተፈሪ የሚገኙ ወንድሞችን አማክሬያቸው ለኦሮሚያ ግብርና ጉዳዩን በማሳወቅና መንገዱን ለመቀየስ በሚደረገው ጥረት ውስጥ የሚወገዱ ዛፎችን ጉዳይ በመነጋገርና ፈቃድ በመውስድ የጥርጊያ መንገዱን ሥራ ከጓደኛዬ ጋር ተመካክረን የምሠራበትን ዶዘር ቦታው ድረስ በመውሰድ እግዚአብሔር የፈቀደልንን ያህል አባቶች በጸሎት እየተራዱን መንገዱን በማስፋትና በመጥረግ ለመኪናም ሆነ ለሰው በቀላሉ መውጣት እንዲያስችል ተደርጓል፡፡” ብሏል፡፡

“ከዚህ በፊት ወደ ገዳሙ ሄጄ አላውቅም፡፡ ጓደኛዬ  ወደዚህ ገዳም ይመላለስ ስለነበር የገዳሙን ችግር ይነግረኝ ነበር፡፡ አብረን ለመሥራት ተነጋግረን የራሴን ግሬደር በማምጣት በመቀየስና ተለዋጭ መንገድ በማዘጋጀት መንገዱን አስተካክለን ለገዳሙ አስረክበናል፡፡ ከዚህ በረከት ልሳተፍ በመቻሌ ተደስቻለሁ” በማለት የገለጸው ደግሞ የ”ዳክ የኮንስትራክሽን ማሽነሪዎች ኪራይ አገልግሎት” ድርጅት ባለቤት ወጣት ክብሮም ተክሌ ነው፡፡

dsc03547ሥራውን ለመሥራት በገዳሙ በቆዩባቸው ጊዜያት ያስተዋሉትን ሲገልጹም “የገዳማውያኑ ስሜት ልዩ ነው፡፡ የገዳማውያን አባቶችና እናቶች ደስታ ተመልክተናል፡፤ እንኳን እነሱ ለዘመናት የተቸገሩት ቀርቶ እኛም የተሰማን ስሜት መግለጽ ከምንችለው በላይ ነው፡፡ ደስታቸው አስደስቶናል፡፡ ሰዎች ለእግዚአብሔር በሰጡ ቁጥር የሚጎድልባቸው የሚመስላቸው አሉ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር የተሻለ ነገር እንደሚሰጣቸው ማመን አለባቸው፡፡ ለእግዚአብሔር መስጠት አያጎድልም ይጨምራል እንጂ፡፡ የእኛን ደስታ ሌሎችም እንዲጋሩት እንፈልጋለን፡፡ ያደረግነው ነገር ትንሽ ቢሆንም ከእግዚአብሔር ጋር ከሆንክ ትረካለህ፡፡ ወደፊትም አቅማችን እያዳበርን ሌሎች ገዳማትን የመርዳት እቅድ አለን፡፡” በማለት ሁለቱ በጎ አድራጊ ወጣቶች ተናግረዋል፡፡

ማኅበረ መነኮሳቱ ስለተከናወነው የመንገድ ሥራ  ሲገልጹ “ብርሃን አየን፡፡ ለዘመናት የተቸገርንበትና ከአቅማችን በላይ የሆነውን ነገር እግዚአብሔር ደብቆ ያስቀመጣቸው ልጆቹን በመላክ አስወገደልን” ብለዋል፡፡

በተያያዘ ዜና ከአሰቦት ከተማ መገንጠያ እስከ ተራራው መውጫ ሥር ድረስ 12 ኪሎ ሜትር የሚፈጅ ሲሆን ገዳሙ ያለበትን የመንገድ ችግር ለመቅረፍ ከሚመለከተው ከክልሉ መንገዶች ባለስልጣን መሥሪያ ቤት ጋር  በመወያየት እንዲሁም አዲስ አበባ ከሚገኙ ምእመናን ጋር በመነጋገር  የመንገድ ሥራውን የሚቆጣጠርና የሚመራ አንድ ኮሚቴ አዋቅሮ በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል፡፡ በዚህም መሠረት በፌደራል መንገዶች ባለሥልጣን ሁሉን አቀፍ ተደራሽነት ያለው የገጠር መንገድ ፕሮግራም (Universal Rural Road Access Program) – URRAP መንገዱን ለመሥራት ባጠናው ጥናት መሠረት እሰከ 6 ሚሊዮን ብር እንደሚፈጅና 1 ሚሊዮን ብር ገዳሙ ከቻለ ቀሪውን ወጪ በመንግሥት እንደሚሸፈን በመግለጹ ስምምነት ላይ በመድረስ ሥራው ሊጀመር ችሏል፡፡

 

“ገዳሙም ባቋቋመው ኮሚቴ መሠረት ገንዘብ ከምእመናን በማሰባሰብ ላይ የሚገኝ ሲሆን የመንገዱ ሥራም የመጀመሪያውን ዙር በማጠናቀቅ ወደ ሁለተኛው ክፍል ተሸጋግሯል፡፡ ሥራውንም በቅርበት በመከታተል ላይ እንገኛለን፡፡ ገዳሙ ገንዘብ ለማሰባበሰብ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ ሲሆን ከምእመናን  የታቀደውን ያህል ለማሰባበሰብ ባይቻልም በተገባው ቃል መሠረት የመጀመሪያ ዙር ክፍያ ተፈጽሟል፡፡ ቀጣዩንም ሥራ ለማከናወን የገንዘብ ማሰባሰቡ ይቀጥላል“ በማለት የኮሚቴው የቴክኒክ ክፍል ሓላፊ የሆኑት ኢንጂነር ዮሐንስ ዘውዴ  ገልጸዋል፡፡

 

በተጨማሪም ማኅበረ ቅዱሳን ገዳሙ ያለበትን የውኃ ችግር ለመቅረፍ በቅርቡ የባለሙያዎች ቡድን በመላክ አጥንቶ መመለሱን ከቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

 

በ13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተገደመው የአሰቦት ደብረ ወገግ ቅድሥት ሥላሴና አቡነ ሳሙኤል ገዳም በተደጋጋሚ የእሳት ቃጠሎ ያጋጠመው ሲሆን እሳቱን ለመጥፋት በተደረገው ጥረት ውስጥ የተራራው አስቸጋሪነት ትልቁ ፈተና እንደነበር ይታወሳል፡፡

ledet04

የድንግሊቱም ስም ማርያም ነበር

ኅዳር 19 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ር ሰሎሞን መኩሪያ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ

ledet04በቤተ እስራኤል ስም ጠባይን፣ ግብርን፣ ሁኔታን እንደሚገልጥ ሁኖ ይሰየማል፡፡ ስለ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም “ማርያም” የሚለውን ስያሜ ከማየታችን በፊት ስለ ድንግል ማርያም አባቶቻችን በነገረ ማርያም ያሉትን ጥቂት እንመለከታለን፡፡ “ነቢዩ ኢሳይያስ በትንቢቱ በም.1፥9 ላይ እንደተናገረ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ዘርን ባያስቀርልን ኖሮ እንደ ሰዶም በሆንን ገሞራንም በመሰልን ነበር፡፡” እንዳለ በኦ.ዘፍ.ም.19፥1 ጀምሮ እንደተጻፈ የሰዶምና የገሞራ ሰዎች በበደላቸው ምክንያት እንደተደመሰሱ /እንደጠፉ/ እናነባለን፡፡ አዳምና ልጆቹ በሲዖል ባህር ሰጥመን እንዳንቀር እግዚአብሔር በቸርነቱ ንጽህት የሆነች ዘር መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስ የሌለባት በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ እያማለደች የምታሰጥ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ባያስቀርልን ከእርሷም መርገመ ሥጋ መርገመ ነፍስን የሚያርቅ በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ የሚያድል የባሕርይ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ተወልዶ በሞቱ ሞታችንን ባይደመስስ ወደ ሕይወት ባይመልሰን ኖሮ መኖሪያችን ሲዖል ነበር፡፡

 

ለፍጥረት ሁሉ መዳን ምክንያት ያደረጋት ንጽሕት ዘር እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትውልዷ በአባቷ በኩል ከንጉሡ ከዳዊት ወገን ነው፡፡ በእናቷ በኩል ከሊቀ ካህናቱ ከአሮን ወገን ነው፡፡ የአባቷ ስም ቅዱስ ኢያቄም የእናቷ ስም ቅድስት ሐና  ይባላል፡፡ ሁለቱም በሕግ በሆነ ቅዱስ ጋብቻ ሲኖሩ ለብዙ ዘመን ልጅ አልነበራቸውም፡፡ ልጅ ይሰጠናል በማለት ተስፋ እግዚአብሔርን በጾም በጸሎት ደጅ እየጸኑ ኖሩ እንጂ፡፡ በዘመኑ ልጅ ያልወለደ ኀጢአተኛ፣ እግዚአብሔር የተጣላው ተደርጎ ይወሰድ ስለነበረ ወደ ቤተ እግዚአብሔር የሚያመጡትን መብዓ አይቀበሏቸውም፤ ይሰድቧቸው፣ ያሽሟጥጧቸውም ነበር፡፡ ይህንን ሁሉ ታግሰው ሲኖሩ እግዚአብሔር ትእግሥታቸውን ተመልክቶ የሚወልዷትን የድንግል ማርያምን ነገር በህልም ገለጸላቸው የእግዚአብሔርን ፈቃድ ሲጠብቁ እመቤታችን ነሐሴ 7 ቀን ተፀንሳለች፡፡ በተፀነሰች ጊዜ ብዙ ተአምራት ተደርጓል፡፡ የሃናን ማሕፀን እየዳሰሱ፡- ብዙ እውራን አይተዋል፣ ድውያን ተፈውሰዋል፣ ምውታን ተነሥተዋል፡፡ ይህንን የተመለከቱ አይሁድ ቅዱስ ኢያቄምን እና ቅድስት ሐናን በድንጋይ ወግረው በእሳት አቃጥለው ሊገድሏቸው በጠላትነት ሲነሡ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ሊባኖስ ወደ ሚባል ተራራ ይዟቸው ወጣ፡፡ በዚያ ሳሉ በግንቦት 1 ቀን ከፀሐይ 7 እጅ የምታበራ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደች፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን በመኀልይ በም.4፥8 ላይ እንደተናገረ “ሙሽራዬ ሆይ ከሊባኖስ ነይ…. ከአንበሶች ጉድጓድ ከነብሮችም ተራራ ተመልከች፡፡” እንዳለ ይህ ትንቢት ተፈጸመ በተወለደች በ8ኛው ቀን ስሟን “ማርያም” ብለው አወጡላት ለመሆኑ ማርያም ማለት ምን ማለት ነው?

 

ሀ. ማርያም ማለት ጸጋ ወሀብት ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት በመዝ.126፥3 ላይ ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታ ናቸው፡፡” ብሎ እንደተናገረ አባቷ ቅዱስ ኢያቄም እናቷ ቅድስት ሐና ከእግዚአብሔር የተሰጠችን ስጦታችን፣ ሀብታችን ናት ብለው “ማርያም” አሏት፡፡ ለጊዜው ለእናት እና ለአባቷ ስጦታ ሁና ትሰጥ እንጂ ለፍፃሜው ለፍጥረት ሁሉ እናት አማላጅ ሆና ከእግዚአብሔር የተሰጠች ናት በተለይ ለክርስቲያኖች በእምነት እናትነቷን እና አማላጅነቷን ለሚቀበሉ በዮሐንስ ወንጌላዊ አማካኝነት እናት ሁና የተሰጠች ልዩ ስጦታ ናት አምላካችን ክርስቶስ በቀራኒዮ አደባባይ በመስቀል ተሰቅሎ ቅዱስ ሥጋውን ቆርሶ ክቡር ደሙን አፍስሶ ለድኅነታችን እንደሰጠን ሁሉ እናቱንም እናት ትሁናችሁ ብሎ ሰጥቶናል፡፡” ዮሐንስ ወንጌላዊ ወደ ቤቱ እንደወሰዳት እኛም ወደ ቤተ ልቦናችን ልናስገባት ጣዕሟን በአንደበታችን ፍቅሯን በልቦናችን ልናሳድረው ያስፈልጋል፡፡ ዮሐ.19፥26 የድንግል ማርያም ጣዕሟ በአንደበታችን ፍቅሯ በልቦናችን ይደር፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልም ከእግዚአብሔር ተልኮ ወደ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም መጥቶ እያመሰገናት እየተሳለማት የነገራት ነገር ቢኖር እርሷ “ምልዕተ ጸጋ ወክብር” እንደሆነች ነው፡፡ ሉቃ.1፥28 እንግዲህ መልአኩ ከእግዚአብሔር አግኝቶ የእመቤታችንን ነገር እንደነገረን የጐደለባት ጸጋ የሌለ እመቤት ናት እና እኛ ደግሞ ብዙ ነገር ጐድሎብናልና ከተትረፈረፈ ጸጋዋ እንድታድለን ምልዕተ ጸጋ ምልዕተ ውዳሴ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ልንማፀናት ይገባል፡፡ እመቤታችን ጸጋ በረከት ታድለን፡፡

 

ለ. ማርያም ማለት ፍፅምት ማለት ነው፡ “ፍፅምት” ማለት እንከንና ጉድለት የሌለባት ማለት ነው፡፡ እመቤታችን ለጊዜው መልክ ከደምግባት ጋር አስተባብራ በመገኘቷ ፍፅምት ተብላለች፡፡ እግዚአብሔር አምላክ በባሕርይው ቅዱስ ነው፡፡ ዘሌ.19፥2 ቅዱስ እና ንፁሐ ባሕርይ የሆነ እግዚአብሔር ዓለምን ለማዳን በወደደ ጊዜ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው እንደተናገረ “እግዚአብሔር በሰማይ ሁኖ ምሥራቁን እና ምዕራቡን ሰሜኑን እና ደቡቡን ዳርቻዎችን ሁሉ ተመለከተ እንዳንቺ ያለ አላገኝም የአንቺን መዓዛ ወደደ፤ ደምግባትሽን ወደደ፤ የሚወደውን ልጁን ወደ አንቺ ሰደደ” እንዲል፡፡ ንፁሐ ባሕርይ እግዚአብሔር ለማደሪያነት /ለተዋሕዶ/ እመቤታችንን መረጠ እርሷም ፍፅምት ናት የአዳም መርገም ያልወደቀባት /ጥንተ አብሶ/ የሌለባት ጠቢቡ ሰሎሞን በመኀል.4፥7 ላይ እንደተናገረ እንዲህ ብሎ “ወዳጄ ሆይ ሁለንተናሽ ውብ ነው ነውር የለብሽም፡፡” እንዲል እንኳን የአምላክ እናት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቀርቶ ወዳጆቹ ቅዱሳን እንኳን አካሄዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር ሲያደርጉ ከፍፁምነት ማዕረግ ይደርሳሉ ይህንንም ቅዱስ መጽሐፍ ይመሰክርላቸዋል፡፡ ለምሳሌ ኖኅ በትውልዱ ጻድቅ ፍፁምም ሰው ነበር  ዘፍ.6፥9፡፡ ኢዮብም ፍጹምና ቅን እግዚአበሔርንም የሚፈራ ከክፋትም የራቀ ነበር ኢዮብ 1፥1፡፡ ይላል፡፡ የኖኅን እና የኢዮብን አምላክ የወለደች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ፍፅምትነቷ አያጠራጥርም፡፡ የድንግል ማርያም ጸጋ በረክት ይደርብን፡፡

 

ሐ. ማርያም ማለት የሕያዋን እናት ማለት ነው፡፡ ዘፍ.3፥20 ላይ “አዳምም ለሚስቱ ሔዋን” ብሎ ስም አወጣ የሕያዋን ሁሉ እናት ናትና፡፡ ይላል በእርግጥ ሔዋን ለሕያዋን ሁሉ ማለትም ለፍጥረት ሁሉ እናት ናት ግን ፍጥረትን ሁሉ አስጐድታለች ማለትም አትብሉ ተብሎ ከእግዚአብሔር የታዘዘውን ዕፀ በለስን በልታ ለባሏ ለአዳም በማብላቷ በሰው ልጆች ላይ የሞት ሞት እንዲመጣ /እንዲፈርድባቸው/ ምክንያት ሁናለች ከእርሷ ምክንያተ ስህተትነት የተነሣ የገነት ደጃፎች ተዘጉ በምትገለባበጥ የኪሩብ ሰይፍ እንድትጠበቅ ሆነ፡፡ ዘፍ.3፥24 በዚህ የተነሣ በሰው ልጆች ላይ 5500 ዘመን ሞት ሰለጠነ፡፡ አዳም ግን “ሔዋንን” የሕያዎን ሁሉ እናት ብሎ በትንቢት የተናገረላት ሔዋንን ሳይሆን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ነው፡፡ ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴ ማርያም ዘሐሙስ “በእንተ ሔዋን ተዐፅወ ኆኅተ ገነት ወበእንተ ማርያም ድንግል ተርኀወ ለነ” ይላል ትርጉሙም “ስለ ሔዋን የገነት ደጅ ተዘጋ ዳግመኛ ስለ ድንግል ማርያም ተከፈተልን” ማለት ነው፡፡ ሔዋን ሕያዋንን ሁሉ አስጐዳች ዳግማዊት ሔዋን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ደግሞ ለሕያዋን ሁሉ እናት ሆና ፍጥረቱን ሁሉ ለማዳን ምክንያት ሆነች፡፡

 

ሕያዋን የሚባሉት ጥምቀተ ክርስትና ያላቸውን ወልድ ዋሕድ ብለው በልጇ በኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት የሚያምኑትን ክርስቲያኖችን ነው፡፡ እነዚህ ሕያዋን  ናቸው፡፡ ጌታ በቅዱስ ወንጌሉ “በወልድ ያመነ የዘለዓለም ሕይወት አለው ያላመነ ግን አሁን ተፈርዶበታል፡፡” እንዲል ዮሐ.3፥37 ደግሞም ሰው ሰው ተብሎ በሕይወት ለመኖር ከእናት ከአባቱ መወለድ ግድ እንዲሆንበት ክርስቲያንም ክርስቲያን ይባል ዘንድ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ በጥምቀት መወለድ አለበት ዮሐ.3፥5፡፡ የእነዚህ እናታቸው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፡፡ አንድም ሕያዋን የሚላቸው ለገነት ለመንግሥተ ሰማያት የሚያበቃቸውን የነፍስ ሥራ ሠርተው በጽድቅ የተሸለሙ ቅዱሳን ጻድቃን ሰማዕታት ናቸው የእነዚህ እናታቸው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ናትና ስማን “ማርያም” አሉት፡፡

 

መ. ማርያም ማለት ከፍጡራን ሁሉ በላይ ከፈጣሪ በታች የከበረች ደግ ፍጥረት ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ የሚታየውንና የማይታየውን ብዙ ፍጥረት ፈጥሯል ከእነዚህ ፍጥረታት መካከል ግን ሰው እና መላእክት ክብሩን እንዲወርሱ ስሙን እንዲቀድሱ ለይቶ ፈጥሮአቸዋል፡፡ ከሰው መላእክት በቅድስና ለእግዚአብሔር የቀረቡ ናቸው፡፡ ከእነዚህ መላእክት መካከል ስድስት ክንፍ ያላቸው ብዙ ዐይኖች ያሏቸው የእግዚአብሔርን ዙፋን የሚሸከሙ እግዚአብሔርም በዘፈቀደ ለወዳጆቹ ሲገለጽ የሚታይባቸው ክብር ያላቸው ናቸው፡፡ በፈጣሪያቸው ፊት ግን ሲታዩ ትእምርተ ፍርሐት አላቸው ከዙፋኑ የሚወጣው እሳት እንዳያቃጥላቸው በሁለት ክንፋቸው ፊታቸውን ይሸፍናሉ፤ ገጽህን ማየት አይቻለንም ሲሉ፤ በሁለት ክንፋቸው ከዳርቻ እስከ ዓለም ዳርቻ ይወጣሉ ይወርዳሉ ባህርይህን ተመራምሮ መድረስ አይቻልም ሲሉ፡፡ እንዲህ ባለ ፍርሐት ፈጣሪያቸውን “ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር ጸባዖት ፍጹም ምሉዕ ሰማያተ ወምድረ ቅድሳተ ስብሐቲከ” እያሉ ያመሰግናሉ፡፡ ራዕ.4፣ ኢሳ.6 እነዚህ ከፍጡራን ሁሉ የከበሩ ለእግዚአብሔርም የቀረቡ ናቸው ከእነዚህ ግን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትበልጣለች፡፡ ምክንያቱም እነርሱ እንዲህ ከሚንቀጠቀጡለት ከሦስቱ ቅዱስ አንዱን ቅዱስ ወልደ እግዚአብሔርን ዘጠኝ ወር ከ5 ቀን በማሕፀኗ የተሸከመች አዝላ የተሰደደች በማስተማር ዘመኑ ያልተለየች እስከ እግረ መስቀል ድረስ የነበረች የአምላክ እናት ናትና ስለዚህም ቅዱስ ኤፍሬም ሲናገር “ይእቲ ተዓቢ እም ኪሩቤል ወትፈደፍድ እም ሱራፌል እስመ ኮነት ታቦተ ለአሐዱ ዘእም ቅድስት ሥላሴ” ብሏል በእውነትም ከኪሩቤል እና ከሱራፌል ትበልጣለች ከቅድስት ሥላሴ አንዱን ወልደ እግዚአብሔርን በሕቱም ድንግልና ፀንሳ በሕቱም ድንግልና ወልዳዋለችና ይህ ጸጋ ለእመቤታችን እንጂ ከፍጡራን መካከል ለሌላ ለማንም አልተሰጠምና ከነገደ መላእክት ከደቂቀ አዳም በክብር የሚመስላት በጸጋ የሚተካከላት የለም፤ ከፍጡራን በላይ ያሰኛታል፡፡ “ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ….. ካንቺ የሚወለደው ቅዱስ ነው፡፡ የልዑል እግዚአብሔርም ልጅ ይባላል፡፡” ሉቃ.1፥28፣ ሉቃ.1፥35 እንዲል፡፡

 

ሠ. ማርያም ማለት መርሕ ለመንግሥተ ሰማያት ማለት ነው /መንግሥተ ሰማያት መርታ የምታስገባ/ ማለት ነው፡፡ የቀደመው ፍጥረት የታደሰባት ወደ ቀደመ ርስቱ ወደ መንግሥተ ሰማያት ለመግባት ምክንያተ ድሂን የሆነችው እመቤታችን ድንግል ማርያም ናት ዛሬም ያለው ፍጥረት ወደ መንግሥተ ሰማያት ለመግባት የድንግል ማርያም ምልጃ ያስፈልገዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን የእመቤታችንን መርቶ መንግሥተ ሰማያት የምታስገባ የመሆኗን ነገር በምሳሌ እንዲህ ስትል ታስተምራለች፡፡ በዘፀ.ም.32 እና 34 ላይ ተጽፎ እንደምናገኘው ሙሴ በደብረ ሲና 40 መዓልት 40 ሌሊት ከጾመ ከጸለየ በኋላ እግዚአብሔር ተቀብሎ ከተራራው ሲወርድ እስራኤል ጣዖት አቁመው ሲሰግዱ ተመለከተ በዚህ ጊዜ ፍቅረ እግዚአብሔር ቢያቃጥለው በፅላቱ ጣዖቱን መታው ፅላቱ ተሰበረ ጣዖቱ ደቀቀ፡፡ ወደ እግዚአብሔር ሲያመለክት ከማይነቅዝ እንጨት ሠርቶ ወደ ተራራው እንዲወጣ በዚያም እንደ ቀድሞው እንዲጾም እንዲጸልይ እግዚአብሔር አዘዘው እርሱም እንደታዘዘው አደረገ እግዚአብሔርም በተሰወረች ጣት ትዕዛዛቱን ጻፈበት ለሙሴም ሰጠው ሙሴም ይህንን ይዞ ከተራራው ሲወርድ ብርሃን ተሳለበት እስራኤል በዚች ፅላት እየተመሩ የዮርዳኖስን ባህር ከፈሉ ኢያሱ.3፥14-17 የኢያሪኮን ቅፅር ናዱ /አፈረሱ/ ኢያ.6፥8 ምድረ ርስት ከነዓን ገብተው ርስት ተካፈሉ፡፡ በዚህ ምሳሌ የቀደመው ከእግዚአብሔር ዘንድ ለሙሴ የተሰጠው የእንቁ ፅላት የአዳም የፅላቱ መገኛ ከእግዚአብሔር እንደሆነ ሁሉ ለአዳምም እናትና አባት መገኛ የሚሆን የለውም ወድቆ መሰበሩ ሕግ ትዕዛዝ በመተላለፉ ከፈጣሪው መለየቱን ያመለክታል፡፡ ፅላቱ እንደተሰበረ ይቅር እንዳላለ አዳምም እንደወጣ ይቅር አላለም በንስሓው ተቀብሎታልና፡፡ ሁለተኛይቱ ፅላት እመቤታችን ሙሴ ሠርቶ መውሰዱ እመቤታችን በዘር መገኘቷን ከቅድስት ሐና ከቅዱስ ኢያቄም መወለዷን ያመለክታል፡፡ ከማይነቅዝ እንጨት መሥራቱ እመቤታችን በሐልዮ /በማሰብ/ በነቢብ /በመናገር/ በገቢር /መሥራት/ ኀጢአት እንዳልፈጸመች ንፅናናዋን ቅድስናዋን ያመለክታል፡፡ በፅላቱ ላይ በእግዚአብሔር ጣት የተጻፈ የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ በማሕፀነ ድንግል የተቀረጸው የአብ አካላዊ ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሆነ ያመለክታል፡፡ ዮሐ.1፥1 “በመጀመሪያ ቃል ነበረ ቃልም እግዚአብሔር ነው” ዮሐ.1፥14 የቃል ሥጋ ሆነ በእኛም አደረ” እንዳለ፡፡ በዚያች ፅላት እስራኤል ባህር እንደተከፈለላቸው፣ ቅፅር እንደተናደላቸው ተመርተው ርስት እንዲወርሱ ጥንተ ጠላታትን ዲያብሎስ ተሸንፎ በእመቤታችን በተሰጣት ቃል ኪዳን አማላጅነት ከገቡ መውጣት ካገኙ ማጣት የሌለባት መንግሥተ ሰማያትን ለመውረስ እድል አገኘን፡፡ ከብዙ በጥቂቱ ከላይ የተጠቀሰውን አልን እንጂ ስለ እመቤታችንስ የተነገረው ብዙ ነው፡፡ የድንግል ማርያም ጣዕሟ በአንደበታችን ፍቅሯ በልቡናችን ይደርብን በአማላጅነቷ ለርሥተ መንግሥተ ሰማያት ታብቃን አሜን፡፡

dn. reda wube

ዲያቆን ረዳ ውቤ አረፉ

ኅዳር 17 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


dn. reda wubeበሲዳሞ  ክፍለ ሀገር፣ ቡሌ ወረዳ በሚገኘው ጎንፈራ ቀበሌ፥ ከወላጅ አባታቸው አቶ ውቤ አብዲና ከእናታቸው ከወ/ሮ መሰለች ተመስገን፥ መጋቢት 5 ቀን 1955 ዓ.ም የተወለዱት ዲ/ን ረዳ ውቤ፤ ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በልዩ ልዩ የሕክምና መስጫ ተቋማት ሲረዱ ቆይተው  በ50 ዓመታቸው ኅዳር 10 ቀን 2005 ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞተ ሥጋ ተለይተው፥ ኅዳር 11 ቀን 2005 ዓ.ም በቡራዩ ፄዴንያ ስመኝ ማርያም ገዳም ሥርዓተ ቀብራቸው ተፈጽሟል፡፡

 

ዲያቆን ረዳ ውቤ ከልጅነት ዕድሜያቸው አንሥቶ ለቤተ ክርስቲያን  ትምህርትና አገልግሎት ከነበራቸው ጽኑ ፍቅር የተነሣ፥ ከመምህራቸው አባ ኀይለ ማርያም ግብረ ዲቁናን ተምረው በ1969 ዓ.ም በወቅቱ የሲዳሞ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከነበሩት ብፁዕ አቡነ በርቶሎሚዎስ መዓረገ ዲቁናን ተቀብለዋል፡፡ከዚህ በኋላ ከ1969 እስከ 1977 ዓ.ም የይርጋለም ደብረ መዊዕ ቅዱስ ሚካኤል ሰንበት ትምህርት ቤትን በመመሥረትና ለአምስት ዓመታት በሰብሳቢነት፣ እንዲሁም ሰንበት ትምህርት ቤቱን በመወከል በደብሩ የሰበካ ጉባኤ በጸሓፊነት አገልግለዋል፡፡ ዲያቆን ረዳ ከ1978 እስከ 1980 ዓ.ም በባሕር ዳር ፖሊ ቴክኒክ ኢንስቲቲዩት በነበራቸው የትምህርት ቆይታ፥ በባሕር ዳር ፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤት በአባልነት ተመዝግበው የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች  ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲሄዱና በሰንበት ትምህርት ቤት እንዲሳተፉ፡ አልፎም ዛሬ በመላ ሀገሪቱ እየተካሄደ ላለው የግቢ ጉባኤ መጀመር ምክንያት ለመሆን የበቁ ሰው ናቸው፡፡

 

በዲ/ን ረዳ ውቤ ሕይወትና በአገልግሎታቸው ዙሪያ ከተዘጋጀው የግለ ሕይወት ታሪካቸው ለመረዳት እንደተቻለው፡- የመጀመሪያዎቹን ክርስቲያኖች የአንድነት ኑሮን መሠረት በማድረግ በተቋቋመው የጽርሐ ጽዮን ዘተዋሕዶ አንድነት ኑሮ ማኅበርን ከጥቅምት 2 ቀን 1990 ዓ.ም ጀምሮ በመቀላቀል ነፍሳቸው ከሥጋቸው እስክትለይ በዚያው ቦታ ቆይተዋል፡፡ በዚሁ ቆይታቸውም ማኅበሩን በልዩ ልዩ ሓላፊነቶች ያገለገሉ ሲሆን ማኅበሩ ባካሄዳቸው 15 ዙር የሰባክያነ ወንጌል ሥልጠናዎች ላይ በመምህርነት ተሳታፊ ሆነዋል፡፡ በተጨማሪም ከ1990 ዓ.ም. ጀምሮ እስከ ዕለተ ረፍታቸው የማኅበሩ የሰባክያነ ወንጌል ማሠልጠኛ ትምህርት ክፍል ሓላፊ በመሆን አገልግለዋል፡፡

 

መላ ዘመናቸውን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሰጡት ዲያቆን ረዳ ውቤ  የሳንባ፣ የልብና የጨጓራ ሕመማቸውን ታግሰው ቤተሰባቸውና ማኅበሩ እንዳይጨነቅ ሕመምተኛ ሳይመስሉ የተጣለባቸውን ሓላፊነት በትጋት ተወጥተዋል፡፡ዲያቆን ረዳ ባለትዳርና የአራት ልጆች አባት ነበሩ፡፡

በእኛ ዘመን ምንጮቻችን እንዳይነጥፉ

ኅዳር  17 ቀን 2005 ዓ.ም.


የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዘርፈ ብዙ መንፈሳዊ አገልግሎት መሠረት የሆኑት፤ የአባቶች ካህናት፣ ሊቃውንት መምህራን፣ ጳጳሳት የአገልጋዮቿ መፍለቂያ፤ ለዘመናት የማይነጥፉ ምንጮች ሆነው የኖሩት አብነት ትምህርት ቤቶቻችን፤ በዚህ ዘመንና ትውልድ ህልውናቸውን ጥያቄ ውስጥ ያስገባ ፈተና እንደተጋረጠባቸው የዐደባባይ ምስጢር ከሆነ ቆይቷል፡፡

 

ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ የሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን አካላት እንዲሁም ቅን አሳቢ እውነተኛ ልጆቿ ሁሉ ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥተው የተግባራዊ መፍትሔው አካል በመሆን ሲንቀሳቀሱም ይታያል፡፡

 

እንዲህም ሆኖ ግን ከጊዜ ወደ ጊዜ ችግሩ እየተደራረበ መጥቶ በወቅቱ መሠረታዊ ለውጥና የተሻለ እድገት የሚያስገኝ መፍትሔ ባለመሰጠቱ የአብነት ትምህርት ቤቶቻችን ፈተና ከፍቷል /ተባብሷል/፡፡

 

የትምህርት አሰጣጥ ሥርዓቱ ጊዜና አካባቢያዊ ሁኔታዎችን ከመንፈሳዊና ቁሳዊ ሀብቶች ጋር በማገናዘብ ዘመኑን የዋጀ እንዲሆን አለመደረጉ፤ በተቀላጠፈና ወጥ በሆነ መንገድ ተደራጅቶ አለመሰጠቱ፤ የአብነት ትምህርት ቤቶች አደረጃጀት የመማሪያ ክፍሎች፣ የትምህርቱ መርጃ መሣሪያዎች፣ መጻሕፍት ወዘተ በፍጹም አለመሟላታቸው፤ የሊቃውንት መምህራኑ የኑሮ ችግርና በቂ መተዳደሪያ ድጋፍ አለማግኘት፤ የደቀ መዛሙርቱ ለረኃብና ለዕርዛት መዳረግ፤ መጠለያ ማጣት፤ የጤና ክብካቤና ትምህርት የሚያገኙበትና በዝቅተኛ ደረጃም ቢሆን የሕክምና አገልግሎት አለመኖር፤ በአንጻሩ ደግሞ ይህንን ሁሉ ችግርና መከራ ተቋቁመው ለዓመታት ደክመው ከሊቃውንት መምህራን አባቶቻቸው የዕውቀት ማዕድ የቀሰሙትን ዕውቀትና ሙያ ለቤተ ክርስቱያኒቱ አገልግሎት የሚያውሉበት የሥራ ዋስትና ማጣታቸው ከሌሎችም ውጫዊ ተግዳሮቶች ጋር ሲደመር ለመማር ማስተማሩ ትልቅ ፈተና ስለሆነ ወዘተ…. አፋጣኝ ተግባራዊ መፍትሔ የሚፈልግ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ሕልውናና ቀጣይነት ላይ የተደቀነ ገሐድ አደጋም ስጋትም ነው፡፡

 

ሁለንተናዊ ፈተናዎቹን በሚፈታ መልኩ መሠረታዊ መፍትሔ በአፋጣኝ ባይታይም፤ ይህንን ችግር በመቅረፍ የአብነት ትምህርት ቤቶቻችንን ከተደቀነባቸው አደጋ ለመታደግ ተስፋ ሰጪ ጥረቶች እየተደረጉ እንደሆነ ይታወቃል፡፡

 

ባለፈው የጥቅምት ወር 2005 ዓ.ም በተካሄደው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ፤ የአብነት ትምህርት ቤቶችን ለማጠናከር የተወሰነው የዐሥር ሚሊዮን ብር በጀት ለችግሩ የተሰጠውን ትኩረት የሚያመለክት፤ ለአስተማማኝ ቀጣይነቱም የተስፋ ብርሃን የሚፈነጥቅ ነው፡፡

 

ይህንን በድርሻው ለማጠናከር በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አማካኝነት፤ “የጥንቱ ከሐዲሱ ጋር በደጃችሁ አለ” በሚል መሪ ቃል ኅዳር 2 ቀን 2005 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ይፋ የሆነው፤ “አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የነጻ ትምህርትና ሥልጠና ዕድል” የአብነት ትምህርቱን ዘመኑን በዋጀ መልኩ በትውልዱ ቀጣይነት እንዲኖረው የሚያስችል መርሐ ግብር ነው፡፡

 

እንዲህ ዓይነቶቹ ተጠቃሽ የመፍትሔ እርምጃዎች ለቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ቀጣይነት ዋስትና ሰጪ ጥረቶች ናቸው፡፡ አፈጻጸማቸውን በተመለከተም የተቀናጀ አሠራር፤ የቅርብ ክትትልና ቁርጠኛ አገልግሎት ይፈልጋሉ፡፡ ችግሩ እየከፋ ከመምጣቱ አኳያም ቀዳሚ ትኩረትና አፋጣኝ የተግባር ክንውን እንደሚያስፈልግ የታወቀ ነው፡፡

 

አብነት ትምህርት ቤቶች ወቅቱና ትውልዱን እንዲሁም አካባቢያዊ ሁኔታዎችን በማገናዘብ ከዘመናዊው ትምህርት ጋር ተቀናጅተው የሚያድጉበትና የሚቀጥሉበትን መፍትሔ መፈለግና በተግባር ማረጋገጥ ለነገ የሚባል ጉዳይ አይደለም፡፡

 

በተለይም በገጠሩ አካባቢ የሕዝቡ የኑሮ ሁኔታና ለአብነት ትምህርቱ ያለው አመለከካከት እየተለወጠ መምጣቱን ተከትሎ ለመምህራኑና ለተማሪዎቹ የሚያደርገው ድጋፍ መቅረት ዐቢይ ችግር ነው፡፡ ይህንን ችግር ተረድቶ መፍትሔ የሚሆኑ ተተኪ አሠራሮችን መቀየስና በአፋጣኝ ተግባራዊ ማድረግ የግድ ይላል፡፡ ደቀመዛሙርቱ የነገይቷን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መስፋፋት ተስፋ አድርገው፤ ለዓመታት በችግርና መከራ ውስጥ እያለፉ በአብነት ትምህርቱ የቀሰሙትን ዕውቀትና ሙያ ይዘው ከተመረቁ በኋላ፤ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ተመድበው መተዳደሪያ አግኝተው ቤተ ክርስቲያንንም የሚያገለግሉበት አስተማማኝ የሥራ ዋስትና ሊሰጣቸው ይገባል፡፡ ዓለም አቀፋዊውንና አካባቢያዊ ሁኔታዎችን የሚገነዘቡበት፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ አጠቃላይ ለውጦችን በማስተዋል በቀላሉ ተረድተው የሚያዘጋጁበትና በነገ አገልግሎታቸው የትውልድ መሪ የምእመናን አለኝታ ሆነው እንዲቀጥሉ የሚያስችሏቸውን ተጨማሪ ትምህርቶች የሚያገኙበትን መንገድ ማመቻቸትና ተግባራዊ ማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡

 

የአብነት ት/ቤቶች ባልተስፋፉባቸው አህጉረ ስብከት የገጠርና ጠረፋማ አካባቢዎችም፤ የወቅቱን ተጨባጭ ሁኔታ ያገናዘቡና በሚገባ የተደራጁ የአብነት ትምህርት ቤቶችን ማቋቋም ያስፈልጋል፡፡ በየአካባቢው ቋንቋ ሊያስተምሩና ሊያገለግሉ የሚችሉ መምህራነ ወንጌልና አገልጋይ ካህናትን ማውጣት (ማፍራት) ቅድሚያ ከሚሰጣቸው ተግባራት አንዱ ነው፡፡

 

አለበለዚያ አገልጋይ ካህናትና መምህራነ ወንጌል በማጣት ከዕለት ወደ ዕለት የሚዘጉት በየገጠሩና በየበረሐው እንዲሁም በየጠረፉ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ቁጥር በከፍተኛ ፍጥነት እየጨመረ መምጣቱ አይቀርም፡፡ ከቤተ ክርስቲያን እቅፍ እየወጡ በሌሎች የሚነጠቁት ምእመናንም ቁጥር የዚያኑ ያህል እየጨመረ እነሱን ለመታደግ አስቸጋሪ ይሆናል፡፡

 

ተተኪ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እያነሱ፣ በየገዳማቱ የሚያገለግሉ እውነተኛ መነኰሳት እየቀነሱ፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም በሁለንተናዊ መንፈሳዊ አገልግሎቷ እየተዳከመች፤ በማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፍ የሚኖራት ተሳትፎ እየጠበበ፤ እስተዳደራዊ መዋቅሯና አሠራሯ ብቃት እያነሰው፤ ምእመናኗም በመንፈሳዊ ሕይወታቸው፣ በዕለት ተዕለት ኑሮአቸውና ማኅበራዊ ግንኙነታቸው የሚያበረታቸው፣ የሚመክራቸው፣ የሚከታተላቸው፣ የሚያጸናቸውና የሚያመላክታቸው እያጡ በዘመኑ ሥልጣኔ የባሕል ወረርሽኝ እየተዋጡ፣ ለማንነት ጥያቄያቸው ምላሽ እያጡ፣ ለሃይማኖታዊና ማኅበራዊ ቀውስ እየተዳረጉ ይመጣሉ፡፡ የዚህ ሁሉ ድምር ውጤት የሚያስከትለውን የከፋ ችግር ከወዲሁ ለመገንዘብ ከሁላችንም የሚሰወር እንዳል ሆነ ይታወቃል፡፡

 

ስለዚህ ዘርፈ ብዙ ለሆነው የቅድስት ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ አገልግሎት መሠረት የሆኑት፤ የሊቃውንቱ፣ የጳጳሳቱ፣ የአገልጋይ ካህናቱ፣ የመምህ ራነ ወንጌሉ ሁሉ መፍለቂያ ምንጮች አብነት ትምህርት ቤቶቻችን በእኛ ዘመንና ትውልድ ሳይነጥፉ እንዲቀጥሉ በተጠናና ችግር ፈቺ በሆነ መንገድ ጥረት የሚያደርጉትን አካላት በሚቻለን ሁሉ በማገዝ ከሁላችንም ተጨባጭነት ያለው ተሳትፎ ይጠበቅብናል፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

abune petros statute

የብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ሐውልት ለጊዜው ከቦታው ይነሣል

ኅዳር 15 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

የአዲስ አበባ ከተማ ትራንስፖርት ችግርን ለመቅረፍ እንዲያስችል በሚዘረጋው የቀላል ባቡር መሥመር ዝርጋታ ምክንያት የብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ሐውልት እንደሚነሣ የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን አስታወቀ፡፡

abune petros statute

አቶ አበበ ምሕረቱ የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን የኮምኒኬሽን አገልግሎት ክፍል ሓላፊ የሐውልቱ መነሣት ያስፈለገበት ዋነኛ ምክንያት ምን እንደሆነ ሲገልጹ “በቀላል ባቡር መስመር ዝርጋታ ምክንያት መንገዱ ከዳግማዊ አፄ ምኒልክ አደባባይ ጀምሮ ወደ አውቶቡስ ተራ የሚወስደው መንገድ አትክልት ተራ ድረስ ባቡሩ በዋሻ ውስጥ ነው የሚያልፈው፡፡ በተጨማሪም የባቡሩ መስመር  ከምኒልክ አደባባይ ወደ ሽሮ ሜዳ ይዘረጋል፡፡ እንደሁም ከአውቶቡስ ተራ ወደ ቅድስት ልደታ ለማርያም የሚታጠፈው መስመር መነሻም ነው፡፡ ስለዚህ በአሁኑ ወቅት ከማዘጋጃ ቤት አጥር ጀምሮ ወደ ትግበራ የተገባበት ሁኔታ ላይ እንገኛለን፡፡ ሥራው ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ሀውልት ሲደርስ ስዊድን አገር የሚገኘውና ከፍተኛ ልምድ ያለው ዓለም አቀፍ አማካሪ ድርጅት ሥራውን በበላይነት የሚቆጣጠረው ሲሆን በሚያስመጣቸው ባለሙያዎች አማካይነት በክብርና በጥንቃቄ ሐውልቱን አንሥቶ የዋሻው ግንባታ እንደተጠናቀቀ አንዲትም ሣ/ሜትር ሳይዛነፍ እንደነበረ በቦታው ላይ በክብር እንዲያስቀምጥ ይደረጋል፡፡ ሐውልቱ የሀገር ቅርስና ሀብት ነው፤ ለዚህም ከፍተኛ ጥንቃቄ የተሞላበት ሥራ ይሠራል፡፡” ብለዋል፡፡

 

ፕሮጀክቱ የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ብቻውን የሚያከናውነው ሳይሆን የአዲስ አበባ የጽዳትና ውበት ኤጀንሲ፤ የአዲስ አበባ ቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን፤ ባሕልና ቱሪዝም ቢሮዎች፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እንዲሁም የሃይማኖት አባቶች ጋር በመሆን እንደሚከናወን የገለጹት የኮርፖሬሽኑ የኮምኒኬሽን አገልግሎት ክፍል ሓላፊው  በጉዳዩ ላይ ሰፊ ውይይት በማድረግ ወደ ትግበራ እንደተገባ አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል፡፡

 

“ሐውልቱ ተነሥቶ የት ነው የሚቆየው?” በማለት ላቀረብንላቸው ጥያቄ ምላሽ ሲሰጡም “ሐውልቱ በክብር ከተነሣ በኋላ ባለሙያዎቹ በሚያቀርቡት ጥናት መሠረት ባለ ድርሻ አካላት ተወያይተው በሚዘጋጀው አስተማማኝና ምቹ ሥፍራ ላይ እንዲቀመጥ ይደረጋል፡፡ በመጨረሻም በክብር ወደ ቦታው ይመለሳል” ብለዋል ፡፡

 

የዳግማዊ አፄ ምኒልክ ሐውልት በተመለከተም ”አሁን ባለው ዲዛይን መሠረት ሐውልቱን ስለማይነካው አይነሣም” በማለት ምላሻቸውን ሰጥተዋል፡፡

 

“ይህንን ጉዳይ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አሳውቃችኋል?” ብለናቸውም “ፕሮጀክቱ የሁላችንም ነው፡፡ የሀገር ነው፡፡ ጉዳዩ ይመለከታቸዋል ለተባሉት አካላት ሁሉ አሳውቀናል፡፡” በማለት የመለሱ ሲሆን ወደፊትም ተቀራርበው እንደሚሠሩ ገልጸዋል፡፡

 

“ሌላ ዲዛይን ለመሥራት ለምን አልተሞከረም?” ላልናቸው ሲመልሱም “ዲዛይኑ ማእከላዊውን መንገድ ይዞ ነው የተሠራው፡፡ ይህንኑ ተከትሎ ይከናወናል፡፡”በማለት መልሰዋል፡፡

 

በመጨረሻም “ሐውልቱ ከተነሣ በኋላ ወደ ቦታው ለመመለሱ ሓላፊነቱን ማነው የሚወስደው?” ብለን ለጠየቅናቸው  “መንግሥት የህዝብን ችግር ለመፍታት በሚያደርገው ጥረት ውስጥ ሁሉም ሀላፊነቱን ወስዶ የሚሰራ ይሆናል፡፡ ባለ ድርሻ አካላቱም የመንግሥትን ሥራ የሚያስፈጽሙ በመሆናቸው ሓላፊነት አለባቸው፡፡ ስለዚህ ሁሉም ሓላፊነት አለበት” ብለዋል፡፡

የማኅበሩ የቴሌቪዥን ፕሮግራም ተራዘመ

ኅዳር 11 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

የማኅበረ ቅዱሳን የኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ዋና ክፍል በኢቢኤስ የቴሌቪዥን መርሐ ግብር ለመጀመር ከፍተኛ ጥረት እያደረገ እንደሚገኝ ይታወቃል፡፡ ነገር ግን በእኛ በኩል ዝግጅታችንን ለመጀመር ዝግጁ ሆነን እየተጠባበቅን የምንገኝ ሲሆን ከኢቢ ኤስ ቴሌቪዥን  በኢትዮጵያና በመካከለኛው ምሥራቅ አገራት የጀመረው ስርጭት ከኅዳር 5 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ ካልታወቀ አቅጣጫ በተደረገ ከፍተኛ የሳተላይት ሲግናል ማዛባትና እቀባ ወይም “ጃሚንግ” እክል እንደደረሰበት አስታውቋል፡፡ በመሆኑም ስርጭቱ እንደተስተካከለ የማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቪዥን መርሐ ግብር የሚቀጥል ሲሆን በትእግሥት እንድትጠባበቁን በአክብሮት እንጠይቃለን፡፡

mikeale

“በመንገድ ላይ እንዳላጠፋህ በፊትህ መልአክ እሰዳለሁ፤” ዘፀ.33፥1-3

ኅዳር 11 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ር ኢዮብ ይመኑ


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ


mikealeበረሃብ ስደት ምክንያት ከከነዓን ወደ ግብፅ የመጡት ሰዎች ከዮሴፍ ጋር ሰባ ነበሩ፡፡ /ሐዋ.7/ በግብፅም በአባታቸው በያዕቆብ ምርቃት ቁጥራቸውም እጅግ በዛ፡፡ ይህም የቁጥራቸው መብዛት ከ1280-1445 ቅድመ ልደተ ክርስቶስ የተነሣውንና ዮሴፍን የማያውቀውን ንጉሥ አስፈራው፡፡ /ዘፀ.1፥8/ ንጉሡም ጠላት ይሆኑብናል ያም ባይሆን ጠላት ቢነሳብን አብረው ይወጉናል በሚል ፍርሃት አገዛዝ በማጥናት በቀን በሌሊት በከባድ ሥራ እየጠመደ በጭካኔ ጡብ እያስገነባ ፊቶም፣ ራምሴ፣ ዖንን የተባሉ ታላላቅ ከተሞችን እያሠራ ኖራ እያስወቀጠ ጭቃ እያስረገጠ በሥራ ደክመው ልጅ እንዳይወልዱና ጉልበታቸውን እየደከመ በጅራፍ አየገረፈ መከራ አጸናባቸው፡፡ ይህን ቢያደርግም ጉልበታቸው እየበረታ ከእርሱ መከራ የአባቶቻቸው ምርቃትና ቃል ኪዳን እየረታ አሁንም ሲበዙ ወንድ ሲወለድ በመግደል እስራኤልን ለመቆጣጠር ሞከረ፡፡ ግን የመከራው ብዛት የሕዝቡም ጩኸት የራሔልም እንባ እግዚአብሔርን፡- “የሕዝቤን መከራ በእውነት አየሁ” አስብሎ በእግዚአብሔር ፈቃድ በቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነት በሙሴ ጸሎት በግብፅ ምድር በ9 መቅሰፍቶች 10ኛ ሞተ በኩር  11ኛ ስጥመተ ባሕር የወጡት እስራኤል ከነዓን ገብተዋል፡፡ ይህም የኅዳር 12 መታሰቢያ በዓል መጽሐፍ ቅዱስ “በመንገድ ላይ እንዳላጠፋህ… በፊትህ መልአክ እሰዳለሁ፤” ዘፀ.33፥1-3 እንዳለ ከመከራ የወጡትን እስራኤል በጉዞአቸው ካለው መሰናከል እየጠበቀ “በመንገድ ላይ” እንዳይጠፉ እያማለደና በምሕረት እየታደገ ከጠላት ሲዋጉ አብሮ እየቀደመ ከዲያብሎስ ተንኮል እየሰወረ እግዚአብሔር ወዳዘጋጀላቸው ሥፍራ ያስገባው “መልአክ” የቅዱስ ሚካኤል መታሰቢያ በዓል ነው፡፡

 

እግዚአብሔር የሰው ልጆችን ድካም የሚያውቅ አምላክ ነው፡፡ የሰው ልጅም የእግዚአብሔርን ውለታ የሚዘነጋ የተደረገለትንም የሚረሳ ፊቱ ባለ ነገር ብቻ የሚጨነቅ ነገ በሚመጣው ብቻ የሚጠበብ እንጂ ትላንትን አስቦ እግዚአብሔርን የሚያመሰግን ባለመሆኑ የሰው ልጅ ትላንት የተደረገለትን እንዳይረሳ ይልቁን ትላንትን እያሰበ እግዚአብሔርን እንዲያመሰግን መጪውን ትውልድ ከትላንት እውነት ጋር እንዲዋሐድ ያለፉት ሥራዎቹ እንዲታሰቡ እንጂ ከቶ እንዲዘነጉ ስለማይፈለግ መታሰቢያን ሰጥቶናል፤ ይህም እኛን በእርግጥ ለመርዳት የተደረጉ ድኅነታችንን ለማገዝ የተሠሩ ሥርዓቶች ናቸው፡፡ መጽሐፍ “መታሰቢያህም ለልጅ ልጅ ነው፡፡…. ይህ ለሚመጣ ትውልድ ይጻፍ፣ የሚፈጠርም ሕዝብ ለእግዚአብሔር እልል ይላል” መዝ.101፥1218 እንዳለ መታሰቢያነቱ የእግዚአብሔርን ሥራ ለማድነቅ ለማመስገን ሆኖ ተጠቃሚውም ከድርጊቱ በኋላ የሚመጣ አዲስ እንግዳ ትውልድ ወደ እግዚአብሔር ማቅረቢያ ለነገ ኑሮ ደግሞ ማዘጋጃና የበረከትም ምክንያቶች ይሆናል መታሰቢያ፡፡ ለዚህ ነው በዳርቷን አጠገብ ባለችው አዳም በምትባል ከተማ የዮርዳኖስን የሞላ ውኃ በእግዚአብሔር ተአምራት ተቋርጦ በደረቅ መሻገራቸውን ለማሰብ “ኢያሱም አላቸው፡- በአምላካችሁ በእግዚአብሔር ታቦት ፊት ወደ ዮርዳኖስ መካከል እለፉ ከናንተም ሰው ሁሉ በእስራኤል ልጆች ነገድ ቁጥር በጫንቃው ላይ አንድ አንድ ድንጋይ ከዚያ ይሸከም፡፡ ይህም በመካከላችሁ ምልክት ይሆናል ልጆቻችሁም በሚመጣ ዘመን የእነዚን የድንጋዮች ነገር ምንድር ነው? ብለው ሲጠይቁአችሁ እናንተ በእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ታቦት ፊት የዮርዳኖስ ውኃ ስለተቋረጠ ነው፤ እነዚህ ድንጋዮች ለእስራኤል ልጆች ለዘለዓለም መታሰቢያ ይሆናል ትሏቸዋላችሁ፡፡” ኢያሱ 4፥4-7 በማለት የመታሰቢያ ዮርዳኖስን በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ የምናገኘው፡ የመታሰቢያ ዕለታት ወይም በዓላት ወይም ምልክቶች ጥቅም ስላላቸው ነው ሥርዓት የተሠራላቸው፡፡ በእነዚህ ዕለታት ሰው እግዚአብሔርን አመስግኖ ከቅዱሳኑ በረከት አግኝቶ ራሱን በቅድስና ሥፍራ አውሎ ቅድስናን ተምሮ ለቅድስና የሚያበቃውን በረከት ያገኛል፡፡

 

እግዚአብሔር ሥራ የሠራበት፣ በጽኑ ተአምራት ሕዝቡን የታደገበት መንገድ እንደ ቀላል በዝምታ የሚታለፍ ሳይሆን መታሰቢያ የሚደረግባቸው ዕለታት ይሆናሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ “ተዘከረ ገብረ ለስብሐቲሁ፡- ለተአምራቱ መታሰቢያ አደረገ” መዝ110፥4 ይላልና፡፡ ይህ ኅዳር 12 እግዚአብሔር በታላላቅ ተአምራት ሕዝቡን ነጻ ያወጣበት ዕለት በመሆኑ የመታሰቢያ በዓል ሆኗል፡፡ እግዚአብሔር በባሕሪው የእርሱ ለሆኑት ቅዱሳን ክብርና ሞገስ የሚሰጥ አምላክ ነው፡፡ ሰዎች የእርሱ የሆኑትን እንዲያከብሩለት የሚፈልግ አምላክም ነው፡፡ ለዚህ ነው “እነሆም መጥተው በእግሮችህ ፊት ይሰግዱ ዘንድ እኔም እንደወደድሁህ ያውቁ ዘንድ አደርጋቸዋለሁ፡፡” ራዕ.3፥9 የሚለው ወዳጆቹን ማክበር እርሱን ማክበር ነው እነርሱን ማሰብ እርሱን ማሰብ ነውና ነው፡፡ “የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሯችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ የኑሮአቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነት ምሰሏቸው ያለው” ዕብ.13፥7 እነርሱን መመልከት እርሱን መመልከት ነው፡፡ ስለዚህም ይህ የከበረ ዕለት በመንገድ ላይ እሥራኤል እንዳይጠፉ በይቅርታ መልአክ በቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነትና ጥበቃ በእርሱም መሪነት ወዳዘጋጀላቸው ሥፍራ ገብተዋልና ለቅዱስ ሚካኤል በቤቱና በቅጽሩ መታሰቢያና ስም ይሰጣቸዋል፤ ምንም እንኳን ቤቱ የእርሱ ቢሆንም መታሰቢያነቱን ለወዳጆቹ ደስ ላሰኙት ይሰጣል፡፡ /ኢሳ.56፥4/ ልዩ ከሆነው ስሙ ጋር ስማቸው አብሮ እንዲነሣ ያደርጋል፡፡ አድሮባቸው ሥራ ሠርቷልና፤ እንዲሁ አይተዋቸውም እንዲታሰቡለት ያደርጋል፡፡ በቤቱም ብቻ ሳይሆን በፊቱም እነርሱ ሲታሰቡ ሲከብሩ ደስ መሰኘት ብቻ ሳይሆን ምንጩ እርሱ፣ ፈቃጅም ራሱ ነው እንዲህ ተብሎ ተጽፏልና እግዚአብሔርን ለሚፈሩ ስሙንም ለሚያስቡ የመታሰቢያ መጽሐፍ በፊቱ ተጻፈ፡፡” ሚል.3፥16 እነርሱ ስሙን በፍጹም አስበዋልና እርሱ እግዚአብሔር ደግሞ ስማቸው በሌሎች /በእኛ/ እንዲታሰብ ፈቅጿል፡፡ ስለዚህ ከዚህ አንጻር ከእስራኤል ዘሥጋ ነጻ መውጣት ጋር “ስሜ በእርሱ ስለሆነ ዘጸ.23፥20 የተባለለት ቅዱስ ሚካኤል መታሰቢያው ሆኖ ይከበራል፡፡

 

የእግዚአብሔር ሠራዊት አለቃ ሆኜ አሁን መጥቼአለሁ እንዲፈጽሙ የረዳቸው ያጸናቸው እርሱ ቅዱስ ሚካኤል ነበር፡፡ ዲያብሎስ በተንኮል የሙሴን መቃብር አሳይቶ ሕዝቡን በአምልኮ ጣዖት ሊጥል ሲያደባ በጣዖት ወድቀው እግዚአብሔርን በድለው እንዳይጠፉ ከፊታቸው ቀድሞ ከዲያብሎስ ስውር ሤራ የጠበቃቸው ይህ ቅዱስ ሚካኤል ነበረ፡፡ ይሁዳ.1፥9 “የመላእክት አለቃ ሚካኤል ግን ከዲያብሎስ ጋር በተከራከረ ጊዜ ስለሙሴ ሥጋ ሲነጋገር” እንዲል፡፡ ዳግመኛም ቀኑን በደመና ዓምድ ከበረሃው ዋዕይ እየጋረደ ሌሊቱን በብርሃን ዓምድ ጨለማውን እያስወገደ ከመሰናክል እያዳነ ከመከራ እየጠበቀ ነጻ አውጥቶአቸዋልና መታሰቢያ ተደርጎለታል፡፡ ዘጸ.23፥20፣ መዝ.33፥7

 

በኦሪት የሶምሶንን አባትና እናት ማኑሄንና እንትኩደንን ልጅ እንደሚወልዱ ያበሠረውን መልአክ “ነገርህ በደረሰ ጊዜ እንድናከብርህ ስምህ ማን ነው?” መኀ.13፥17 ማለቱ በምስጋናና በደስታ ቀናቸው ይህን ተአምራት ያሳያቸውን መልአኩን ለማክበርና መታሰቢያ ለማድረግ ትውፊት መኖሩን በሚገባ ያሳያል፡፡ ይህ የደስታና የምስጋና ቃል የሚያሰማበት ቀን ደግሞ በዓል ይባላል፤ በዓልም ይሆናል፡፡ መጽሐፍ “በዓል የሚያደርጉ ሰዎች የደስታ የምስጋና ቃል አሰሙ” መዝ.41፥5 ይላልና እኛም በዚህ ዘመን እግዚአብሔር አድሮባቸው ሥራ የሠራባቸውን ተአምራቱን የገለጸባቸው ቅዱሳን፣ ጻድቃን፣ ሰማዕታትና መላእክት የመታሰቢያ በዓል አድርገን በደስታና ከምስጋና ቃል ማክበራችን ፍጹም አምላካዊና መንፈሳዊ መንገድ መሆኑን አምነን እንመሰክራለን፡፡ “ቀንን የሚያከብር ለጌታ ብሎ ያከብራል” ተብሏልና፡፡ ሮሜ 14፥6

ማእከላቱ ጠቅላላ ጉባኤያቸውን አካሄዱ

ኅዳር 11 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን  ማኅበረ ቅዱሳን  የአሰላ፣ የአምቦ፣ የፍቼ፣ የደብረ ብርሃን፣ የወሊሶ እንዲሁም የወልቂጤ ማእከላት ከጥቅምት 25  እስከ ኅዳር 2 ቀን 2005 ዓ.ም ባሉት ጊዜያት ጠቅላላ ጉባኤያቸውን ከወረዳ ማእከላት፣ ከግንኙነት ጣቢያዎች፣ ከግቢ ጉባኤያት የተወከሉ አባላት፣ የየሀገረ ስብከቱ ተወካዮች፣ የወረዳ ሊቃነ ካህናት፣ የአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ተወካዮች እና  የማኅበረ ቅዱሳን የዋናው ማእከልና የመሐል ማእከላት ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ልዑካን በተገኙበት አካሂደዋል፡፡

 

ለጉባኤያቱ በወጣው  መርሐ ግብር መሠረት በ2004 ዓ.ም  ማእከላቱ ያከናወኗቸው የዕቅድ ክንውን ዘገባዎች የቀረቡ ሲሆን፤ በዘገባዎቹ ላይ ውይይት እና አስተያየት ተሰጥቷል፡፡ በሌላ በኩል የማኅበሩን የአራት ዓመት ስልታዊ ዕቅድ መፈጸም ይቻል ዘንድ የማእከላቸውን ነባራዊ ሁኔታ ባማከለ የየራሳቸውን  ድርሻ በመውሰድ አጽድቀዋል፡፡

በአሰላ ማእከል ጠቅላላ ጉባኤ ላይ በመገኘት የማኅበረ ቅዱሳን መልእክት ያቀረቡት ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም ናቸው፡፡ ጠቅላላ ጉባኤው በተመረጡ የመወያያ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ውይይት አድርጓል፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይ የወረዳ ማእከላት የልምድ ልውውጥ አካሂደዋል፡፡ የማእከሉ የ2005 ዓ.ም ሥራ እና የበጀት ዕቅድ ቀርቦ አሳብ ከተሰጠበት በኋላ ጸድቋል፡፡ በመርሐ ግበሩ ፈጻሜ ላይም ከዋና ማእከል የተገኘውን የንዋያተ ቅዱሳት እርዳታ ለገጠር አብያተ ክርስቲያናት ታድሏል፡፡

በተያያዘ ዜና፥ የአምቦ ማእከል የራሱን ጽሕፈት ቤት ለማስገንባት ያዘጋጀውን የመነሻ አሳብ፥ ጉባኤው ሰፊ ውይይት ካካሄደበት በኋላ፤ የቀረበውን አሳብ በማጽደቅ ዝርዝር አፈጻጸሙን የሥራ አስፈጻሚው እንዲመለከተው ወስኗል፡፡ በስልታዊ ዕቅድ ዘመኑም የግንባታው 5% ለመፈጸም መታቀዱን ከማእከሉ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር

ኅዳር 10 ቀን 2005 ዓ.ም.

ሊቀ ልሣናት ቀሲስ ከፍያለው ጥላሁን

ሥነ ምግባር፡- ማለት ደግነት፣ በጎነት፣ መልካም ጠባይ ማለት ሲሆን ክርስቲያን የሚለው ቃል ሲጨመርበት ደግሞ የተሟላና የተለየ ያደርገዋል፡፡ መልካም ጠባይ ማንም ሰው ሊኖረው ይችላል፡፡ ነገር ግን የተሟላ ዘላቂና የሁል ጊዜ ሆኖም ለሰማያዊ መንግሥት የሚያበቃው በክርስትና እምነት ሲኖሩ ነው፡፡

ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር፡- በምድር እያለን ሰማያዊ ኑሮ ኖረን ለሰማያዊ መንግሥት የምንበቃበት ሕይወት ነው፡፡ ሰውን ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔርን ማስደሰት ነውና፡፡ በመሆኑም ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር በሚከተሉት ሕግጋት ሊለካ ይችላል፡፡

 

1.    ሕገ እግዚአብሔር

መጀመሪያውና ዋነኛው የክርስቲያን ሥነ ምግባር መለኪያው ቃለ እግዚአብሔር ነው፡፡ አንድ ሰው ምናልባትም ሕይወቱ በሰው ፊት ሲታይ የማያስደስት በአፍአ ያለው ጠባዩ እንከን የማይወጣለት ሊሆን ይችላል፡፡ በሕገ እግዚአብሔር ተመዝኖ ካላለፈ ዋጋ የለውም በሰው ፊት መልካም ሆኖ የሚታይ ምግባር እግዚአብሔርን ሊያስደስት ያስፈልጋል፡፡ “የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚያደርጉ እንደ ክርስቶስ ባሪያዎች እንጂ ለሰው ደስ እንደምታሰኙ ለታይታ የምትገዙ አትሁኑ፡፡” ፌፌ.6፥6

 

ፈሪሳውያን ከእነርሱ ውጪ የሆነውን ሁሉ የናቁ ያለእኛ ሕገ እግዚአብሔርን አክባሪ ከእኛም በላይ ጻድቅ የለም ባዮች ነበሩ፡፡ ነገር ግን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግብዞችና ሥራቸው ሁሉ ከንቱ እንደሆነ ነገራቸው፡፡ እንዲያውም “ጽድቃችሁ ከጻፎችና ከፈሪሳውያን ጽድቅ ካልበለጠ ወደ መንግሥተ ሰማያት ከቶ አትገቡም” ማቴ.5፥20 በማለት ደቀ መዛሙርቱን አስጠነቀቀ፡፡ እንዲያውም ከእነርሱ እርሾ /ትምህርት/ እንዲጠበቁ አስጠነቀቃቸው፡፡ “ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውያን እርሾ ተጠንቀቁና ተጠበቁ” ማቴ.16፥6 አለ፡፡ ከዚህም ሌላ ብዙ ሠርተናል ሥነ ምግባራችን አስደሳች ነው እያሉ ለመወደስ በኩራት ይቀርቡ የነበሩትን ሁሉ አፍረው እንዲመለሱ አድርጓል፡፡ ማቴ.19፣16-22

 

የንጉሥ ሳዖል ሥራ በራሱ በንጉሡ አሳብ ሲመዘን ምክንያታዊና ትክክልም ነበር፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔርን ሊያስደስት አልቻለም፡፡ ቃሉን ስላላከበረ ለእርሱም ስላልታዘዘ ንቀኸኛልና ንቄሃለሁ ተባለ፡፡ ከንግሥናውም ወረደ፡፡ 1ሳሙ.15፥10-22 “ያለ እምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት አይቻልም፡፡” ዕብ.11፥6

 

ክርስቲያን በጉዞው ሁሉ በጭፍን በራሱ እውቀት ብቻ አይመራም፡፡ በቃለ እግዚአብሔር ሕይወቱን እየመዘነ ሊራመድ ያስፈልጋል፡፡ “በሃይማኖት ብትኖሩ ራሳችሁን መርምሩ ራሳችሁን ፈትኑ፡፡” 2ቆሮ.13፥5 የክርስትና እምነት እያጸኑና እየጠነከሩ እየበሰሉ የሚጓዙበት ሕይወት ነው፡፡ በመሆኑም አንድ ክርስቲያን ከትላንት ዛሬ ከአምና ዘንድሮ አድጐ ጠንክሮ መገኘት አለበት፡፡ “ንቁ በሃይማኖት ቁሙ ጐልምሱ ጠንክሩ” 1ቆሮ.16 በሃይማኖት መጠንከር ሲባል በጊዜውም /በተመቸ ጊዜ/ አለ ጊዜውም /ባልተመቸ ጊዜ/ መጠንከር ይገባል፡፡ “በጊዜውም አለ ጊዜውም ጽና፡፡” 2ጢሞ.4፥2 እንዲል፡፡

 

ከሰው ሕግ ይልቅ የእግዚአብሔር ሕግ ቅርብ ነው፡፡ ከሰው ሕግ መደበቅ መሸሽ ይቻላል፡፡ ከእግዚአብሔር ግን ማምለጥ አይችልም፡፡ የእያንዳንዱ ሰው ሥራ በእርሱ ዘንድ የተገለጠች ናት፡፡ የጲጥፋራ ሚስት ዮሴፍን ማንም አያየኝም ኀጢአት እንሥራ ብላ ለሁለት ዓመታት ባባበለችው ጊዜ ኩፋ.27፥25 እግዚአብሔር ከእርሱ እንደማይለይ እያንዳንዱም ሥራው በፊቱ የተገለጠ እንደሆነ ያመነው ኀጢአትን እንዴት እሠራለሁ በማለት መለሰለት፡፡ ዘፍ.39፥9፣ መዝ.138፥2-12

 

ስለዚህ ክርስቲያናዊ አኗኗራችን መልካም ምግባራችን ትክክለኛ የሚሆነው በእግዚአብሔር ሲመዘን ብቻ ነው፡፡ ብልጣሶርን “በሚዛን ተመዝነህ ቀለህ ተገኘህ” ዳን.5፥27 የተባለው ለዚህ ነው፡፡ የሰው ልጁ ሕግ ተለዋዋጭና ጊዜያዊ ነው፡፡ ሕገ እግዚአብሔር ግን በዘመናት ብዛት የማይሻርና ቋሚ በመሆኑ ምግባራችን ከዚህ አንጻር ሊለካ ያስፈልጋል፡፡ “እንደ ሥጋ ፈቃድ የሚኖሩ የሥጋን ነገር ያስባሉና እንደ መንፈስ ፈቃድ የሚኖሩ ግን የመንፈስን ነገር ያስባሉ፡፡ ስለ ሥጋ ማሰብ ሞት ነውና ስለ መንፈስ ማሰብ ግን ሕይወትና ሠላም ነው፡፡” ሮሜ.8፥5‐6

 

2.    ሕገ ልቡና

እግዚአብሔር የሰውን ልጅ ሲፈጥረው ከሌሎች ፍጥረታት በተለየ ሁኔታ የሚመራመር ክፉና በጎውን ለይቶ የሚያውቅ አእምሮ ሰጥቶታል፡፡ “ግሩምና ድንቅ ሆኜ ተፈጥሬአለሁና አመሰግንሃለሁ፡፡” መዝ.139፥10 እንዲል፡፡ በተጨማሪም “ሕግህ ለእግሬ መብራት ለመንገዴ ብርሃን ነው፡፡”መዝ.118፥105 ብሏል፡፡ ሕግ ለሙሴ ከመስጠቱ በፊት ደጋግ አባቶች በዚህ ሕግ እየተመሩ እንደሚገባ ኖረዋል፡፡

 

የሰው ልጅ ማንም ባያስተምረውና ባይነግረው የሚጠቅመውንና የሚጎዳውን ያውቃል፡፡ “እያንዳንዱ ሰው ባልንጀራውን እያንዳንዱም ወንድሙን እግዚአብሔርን እወቅ ብሎ አያስተምርም ከታናሹ ጀምሮ እስከ ታላቁ ድረስ ሁሉ ያውቁኛልና ይላል እግዚአብሔር፡፡” ኤር.31፥34 ምሳሌ አቤል “ከበጎቹ በኩራትና ከላቡ አቀረበ፡፡ እግዚአብሔርም ወደ አቤልና ወደ መሥዋዕቱ ተመለከተ ወደ ቃየል እና ወደ መሥዋዕቱ ግን አልተመለከተም፡፡” ዘፍ.4፥4-5 ሄኖክ “አካሄዱን ከእግዚአብሔር ጋር ስላደረገ አልተገኘም እግዚአብሔር ወስዶታልና፡፡” ዘፍ.5፥24 ኖኅ “ኖኅ ግን በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ አገኘ በትውልዱ ጻድቅ ፍጹምም ሰው ነበረ ኖኅ አካሄዱን ከእግዚአብሔር ጋር አደረገ፡፡” ዘፍ.6፥9 እነዚህና ሌሎችም በሕገ ልቡና ተመርተው መልካም ተግባር የፈጸሙና እግዚአብሔርም ሥራቸውን የወደደላቸው ናቸው፡፡ ዕብ.11፥4-7

 

የሰው ልጅ ከእግዚአብሔር በራቀ ቁጥር ግብሩ ወደ እንስሳነት ይለወጥና የሚወቅሰው ኅሊና እንኳን ያጣል፡፡ “የሰው ልጅ ክቡር ሆኖ ሳለ አያውቅም እንደሚጠፉ እንስሶች መሰለ፡፡” መዝ.48፥12 ናቡከደነፆር በበደል ላይ በደል በመጨመሩ ለእግዚአብሔር ሕግ አልገዛም በማለቱ ግብሩ ሁሉ የእንስሳ ሆነ፡፡ ዳን.4፥32 ስለዚህ ክርስቲያን በመጽሐፍ ከተዳፈነው የእግዚአብሔር ሕግ በተጨማሪ በልቡናው ለተቀረጸው ሕግ ይገዛል፡፡ ራሲንም እየመረመረ ይጓዛል አጥፍቶም እንደሆነ ማንም ሳይፈርድበት በራሱ ላይ ይፈርዳል፤ ንስሐ ይገባል የጠፋው ልጅና በጌታ ቀኝ የተሰቀለው ወንበዴ ለዚህ ምስክር ይሆኑናል፡፡ ሉቃ.15፥11-19፣ ሉቃ.23፥41

 

3.    የሰው ሕግ

ይህን በሁለት ከፍሎ መመልከት ይቻላል፡፡ የመጀመሪያው የአንድ ሀገር መንግሥት ወይም የሚያስተዳድር አካል ሕዝቡን ለማስተዳደር የሚያወጣው ሕግ ከሆነ ሁለተኛው ደግሞ ኅብረተሰቡ በባሕሉ ትክክል ነው ብሎ የተቀበለውና በወረቀት ያልተጻፈው ሕግ ነው፡፡ “በቃላችንም ቢሆን ወይም በመልእክታችን የተማራችሁትን ወግ ያዙ” 2ተሰ.2፥15 እንዲል፡፡

 

ክርስቲያን ለእግዚአብሔር ሕግ እንደሚገዛ ሁሉ የሰውንም ሕግ ከእግዚአብሔር ጋር እስከ አላጣላው ድረስ ሊያከብር ይገባል፡፡ አንድ ሰው ምንም ብጾም ብጸልይ፣ ለእግዚአብሔር እገዛለሁ ቢል የሚያስተዳድረውን አካልና የኅብረተሰቡን መልካም ባሕል ካፈረሰ ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባሩን ጎደሎ ያደርገዋል፡፡ በሥራ ቦታ የታዘዘውን ካልፈጸመ፣ የሥራ ሰዓት ካላከበረ፣ በቤተ ክርስቲያን ያለውን ምግባሩን በሌላ ሥፍራ ካልገለጸው ዋጋ አይኖረውም፡፡ ለእግዚአብሔር እንደሚገዛ ሁሉ በሰውም ፊት ያለነቀፋ ሊኖር  ያስፈልጋል፡፡ “በመጥፎና በጠማማ ትውልድ መካከል ያለነቀፋ የዋሆችም ነውርም የሌለባቸው የእግዚአብሔር ልጆች እንድትሆኑ ሳታንጐራጉሩ ክፉም ሳታስቡ ሁሉን አድርጉ በእነርሱም መካከል የሕይወት ቃል እያቀረባችሁ በዓለም እንደ ብርሃን ትታያላችሁ” ፊል.2፥15

 

ሐዋርያው ከዚህም በተጨማሪ “ማንም እንዳይነቅፈን እንጠነቀቃለን በእግዚአብሔር ፊት ብቻ ያይደለ ነገር ግን በሰው ፊት ደግሞ መልካም የሆነውን እናስባለን” ብሏል፡፡ 2ቆሮ.8፥20 ይህ ሲባል ኀጢአትም ሲሆን የሰው ሕግ ወይም ባሕል ነውና ሁሉን መፈጸም አለበት ማለት እንዳልሆነ ሊታወቅ ያስፈልጋል፡፡

 

ለምሳሌ ከአንድ በላይ ማግባት፣ ጫት መቃም፣ ዋርሳ መያዝ፣ ባሕል በሆነበት አካባቢ የሚኖር ክርስቲያን ከሰው ጋር ለመኖር በሚል ሰበብ ይህንና ይህን የመሰለ የአረማውያኑን ኑሮ ይኑር ማለት አይደለም፡፡ እንዲያውም ክርስቲያን በእንዲህ ዓይነት ሰዎች መካከል ሲኖር የቅድስናን ሕይወት በተግባር በመኖር ማንነቱን ሊገልጥ ያስፈልጋል፡፡ “መልካሙን ሥራችሁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችሁን እንዲያከብሩ ብርሃናችሁ እንዲሁ በሰው ፊት ይብራ፡፡” ማቴ.5፥16

 

ከዚህ አንጻር ብዙ ወጣቶች ሕገ እግዚአብሔርን ከኑሮአቸው ጋር አጣጥመው መጓዝ ሲከብዳቸው ይታያሉ፡፡ በእምነት የጸኑትን ሠለስቱ ደቂቅን፣ ዮሴፍን ሶስናን አይመለከቱም፡፡ እንኳን ክርስቲያን የሚለውን ስም የተሸከሙ ሲጠራም የሰሙት የማይመስሉ አሉ፡፡ ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር በሰውና በእግዚአብሔር ፊት የምንኖረው ኑሮ እንደመሆኑ መጠን የግል መንፈሳዊ ሕይወትና ማኅበራዊ ኑሮ በማለት በሁለት ከፍለን መመልከት እንችላለን፡፡

 

ሀ. የግል መንፈሳዊ ሕይወት፡-

የግል መንፈሳዊ ሕይወት ማለት እኛ ሰዎች በእግዚአብሔር ፊት የሚኖረን ሕይወት ነው፡፡ ይህም ከእግዚአብሔር ጋር በሚኖረን ግንኙነት ይመሠረታል፡፡ አንድ ሰው ፍቅሩ እግዚአብሔር ከሆነ ምግባሩ መንፈሳዊ ሕይወቱ ይህንኑ የሚገልጥ ይሆናል፡፡ አንድ ሰው ከእግዚአብሔር ጋር የሚኖረው ሕይወት የጠበቀ ለማድረግ ከሚያስፈልጉት ነገሮች ውስጥ ቃለ እግዚአብሔር፣ ንስሓ፣ ቅዱስ ቁርባን፣ ጸሎት ወሳኝ ነገሮች ናቸው፡፡

 

ቃለ እግዚአብሔር ለአንድ ክርስቲያን የሕይወት መስመሩን የሚያቃናለት ነው፡፡ “ቃልህ ተገኝቷል እኔም በልቸዋለሁ አቤቱ የሠራዊት ጌታ ሆይ በስምህ ተጠርቼአለሁና ቃልህ ሐሴትና የልብ ደስታ ሆነኝ፡፡” ኤር.15፥16

 

ንስሓ ማለት መጸጸት ማለት ነው፡፡ የክርስትና ሕይወት የንስሓ ሕይወት ነው፡፡ በንስሓ የበደለ ከበደሉ ይነዳል፡፡ ኀጢአተኛውም ጻድቅ ይሆናል፡፡ ስለዚህ ለግል መንፈሳዊ ሕይወት ሥራችሁን አቅኑ፡፡” ኤር.18፥11 ከንስሐ በኋላ ቅዱስ ቊርባን መቀበል ያስፈልጋል፡፡ “የሰውን ልጅ ሥጋ ካልበላችሁ ደሙንም ካልጠጣችሁ ሕይወት የላችሁም፡፡” ዮሐ.6፥53

 

እንግዲህ ቃሉን ሰምተን ንስሓ ገብተን ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ስንቀበል የግል መንፈሳዊ ሕይወታችን የተስተካከለ ይሆናል፡፡ የግል መንፈሳዊ ሕይወት ጽናት ደግሞ ለማኅበራዊ ኑሮአችን ወሳኝ ነውና፡፡ “ማደግህ በነገር ሁሉ እንዲገለጥ ይህን አሳብ ይህንም አዘውትር፡፡ ለራስህና ለትምህርትህ ተጠንቀቅ፡፡ በእነዚህ ጽና ይህን ብታደርግ ራስህንም የሚሰሙህንም ታድናለህ፡፡” 1ጢሞ.4፥15

 

ለ. ማኅበራዊ ኑሮአችን

ክርስቲያን በማኅበራዊ ኑሮው ከሌሎች ጋር በሠላምና በፍቅር ሊኖር እንዲሁም አልጫውን ዓለም በምግባሩ ሊያጣፍጥ ይገባል፡፡ በመሆኑም ክርስቲያን በማኅበራዊ ኑሮ ተሳትፎ ውስጥ ሊይዝ  የሚገባቸው ነገሮች አሉ፡፡ እነዚህም፡-

 

ዓላማ፡- ክርስቲያን እንደ ውኃ ላይ ኩበት እየተንሳፈፈ ወንዙ ወደ ሚወርድበት አቅጣጫ አይጓዝም፡፡ እንደሚወዛወዝ ዛፍም ወደ ነፈሰበት አያጋድልም፡፡ የራሱ የሆነ ውሳጣዊ ዓላማና አቋም አለው፡፡ “በምትሄድበት ሁሉ እንዲከናወንልህ ወደ ቀኝም ወደ ግራም አትበል፡፡” ኢያሱ.1፥7 ከዚህ የተነሣ የሚሠራውን በጽናትና በትጋት ይሠራል፡፡ የጀመረውን ከፍጻሜ ያደርሳል፡፡ በመከራ አይናወጥም፡፡ መስሎ ለማደር እንደ ጊዜው አይለወጥም፡፡ በዓላማ ስለሚጓዝ ዓላማውን ያሳካል፡፡

 

ክርስቲያን ምን ዓይነት ዓላማ ሊኖሩት ያስፈልጋል?

መንግሥተ ሰማያትን መውረስ፡- አንድ ክርስቲያን ወደ እግዚአብሔር ቤት የሚመጣው ለጊዜያዊ ችግሩ ብቻ መፍትሔ ለማግኘት አስቦ ሳይሆን ሰማያዊ ክብርና ዋጋ ለማግኘት ነው፡፡ “ድንኳን የሆነው ምድራዊ መኖሪያችን ቢፈርስ በሰማይ ያለ በእጅ ያልተሠራ የዘለዓለም ቤት የሚሆን ከእግዚአብሔር የተሠራ ሕንፃ እንዳለን እናውቃለን፡፡ 2ቆሮ.5፥1

 

የሚታወቅና ግልጽ ዓላማ፡- ክርስቲያን ያለ ዓላማ በጭፍን አይጓዝም፡፡ ሳይታሰብ በድንገት በአጋጣሚ የሚል ነገር በርሱ ዘንድ እምብዛም ቦታ አይኖረውም፡፡ የሚታወቅ ግልጽ ዓላማ ኖሮት እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ እንዲሳካለት ይጸልያል፡፡ “ሳታቋርጡ ጸልዩ፡፡” 1ተሰ.5፥18 ከዚህ አንጻር አንዱን ዓላማው አድርጎ ይጓዛል ጋብቻ ወይም ምንኩስና መካከል ሆኖ አያወላውልም፡፡

 

ራስን መግለጽ፡- ክርስቲያን በሄደበት ሁሉ ማንነቱን መግለጥ አለበት፡፡ በተራራ ላይ ያለች ከተማ መሰወር አትችልም፡፡ ይህም ሲባል እኔ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ክርስቲያን ነኝ እያለ በማወጅ ወይም በማስታወቂያ ሳይሆን አኗኗሩ ማንነቱን ይገልጠዋል፡፡ ይህም ኑሮው በቤተሰብ፣ በት/ቤት፣ በሥራ ቦታ፣ በአካባቢው ኅብረተሰብ ዘንድ ወዘተ…… መገለጥ አለበት፡፡

 

ታማኝነት፡- እውነተኛ ክርስቲያን ምሎ የማይከዳ፣ አደራ የማያጠፋ፣ የማያወላውል ለምስክርነት የሚበቃ ነው፡፡ ታማኝ ሰው መልካም የሚለውን ይናገራል፡፡ የሚናገረውን ይሠራል በሓላፊነት ቢቀመጥ ያለ አድልዎ ወገናዊነት ያስተዳድራል፡፡ “በጥቂቱ ታምነሃል በብዙ እሾምሀለሁ፡፡” ማቴ.25፥21 ይባልለታል፡፡ ታማኝነት ለራስ ታማኝ መሆን ለእግዚአብሔር ሰዎች በመታመን ይገለጣል፡፡ ይህም በትዳር፣ በሥራ፣ በተሰጠው ሓላፊነት መታመን አለበት፡፡ ምሳሌ ዮሴፍ ዘፍ.39፥9

 

ፍቅር፡- ክርስቲያናዊ ፍቅር የያዘ ሰው በሰውና በእግዚአብሔር ፍቅር ያለነቀፋ ይኖራል፡፡ ፍቅር የክርስቲያንነታችን መገለጫ ነው፡፡ አምላክን ከዙፋኑ ያወረደው ራሱንም እስከ ሞት አሳልፎ ለሰው ልጅ እንዲሰጥ ያደረገው ፍቅር ነው፡፡ ስለዚህ አንደ ሰው ፍቅር ከሌለው ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር የለውም ማለት ይቻላል፡፡ የምናፈቅረው ማንን ነው?

 

እግዚአብሔርን፡- እግዚአብሔርን ማፍቀር ሲባል እግዚአብሔርንና የእርሱ የሆነውን ሁሉ ማፍቀር ማለት ነው፡፡ ከዚህ አንጻር ፍቅረ እግዚአብሔርን በሁለት ከፍለን ማየት እንችላለን፡፡

 

  1. ትእዛዙን ማክበር፡- እግዚአብሔርን መውደድ ትእዛዛቱን በመፈጸም ይገለጣል፡፡ “ትእዛዙ በእርሱ ዘንድ ያለችው የሚጠብቃትም የሚወደኝ እርሱ ነው፡፡” ዮሐ.14፥21

  2. የእግዚአብሔር የሆነውን ሁሉ መውደድ ይህን በሦስት ከፍለን መመልከት እንችላለን

2.1.    ቅዱሳንን መውደድና ማክበር፡- ቅዱሳን እግዚአብሔር የመረጣቸው ያከበራቸውና የወደዳቸው ናቸው፡፡ “የልጁን መልክ እንዲመስሉ አስቀድሞ ደግሞ ወስኗልና አስቀድሞ የወሰናቸውን እነዚህን ደግሞ ጠራቸው የጠራቸው እነዚህን ደግሞ አጸደቃቸው ያጸደቃቸው እነዚህን ደግሞ አከበራቸው፡፡” ሮሜ.8፥29 ፍቅረ እግዚአብሔር የእርሱ የሆኑ ቅዱሳንን በማክበር እንገልጻለን፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ፍቅር የትሕትናና የኦርቶዶክሳዊነት ውጤት ነው፡፡

2.2.   ሀገርን መውደድ፡- ሀገር የእግዚአብሔር ስጦታ ነው፡፡ አንድ ክርስቲያን እግዚአብሔር በሰጠው ሀገር ሆኖ እርሱን ሊያመሰግን ሀገሩን ሊወድ ግዴታ አለበት፡፡ ሀገር ከሌለ ሠላም ካልሆነ እግዚአብሔርን በደስታ ማመስገን አይቻልምና፡፡ “ኢየሩሳሌም ሆይ ብረሳሽ ቀኜ ትርሳኝ ባላስብሽ ምላሴ በጉሮሮዬ ይጣበቅ ከደስታዬ ሁሉ በላይ ኢየሩሳሌምን ባልወድ፡፡” መዝ.136፥5

2.3.   ቤተሰብን መውደድ፡- ክርስቲያን እምነትን፣ ምግባርን፣ ሥርዓትን በመጀመሪያ የሚማረው ከቤተሰቡ ነው፡፡ ቤተሰብ የመጀመሪያዎቹ ትምህርት ቤቶች ናቸው፡፡ ነቢዩ ሙሴ የእግዚአብሔርን፣ የወገንን፣ የሀገርን ፍቅር የተማረው ከእናቱ ነውና፡፡ ወልደው፣ አሳድገው፣ አስተምረው ለትልቅ ደረጃ ያበቁትን ቤተሰቡን ክርስቲያን ሊወድ ይገባዋል፡፡ “ስለ ቤተሰቦቹ የማያስብ ማንም ቢኖር ሃይማኖትን የካደ ከማያምን ሰው ይልቅ የከፋ ነው፡፡” 1ጢሞ.5፥8

3.   የሰው ልጆችን ሁሉ ማፍቀር፡- /ፍቅረ ቢጽ/ የሰውን ልጅ ሁሉ ማፍቀሩ ፍቅረ ቢጽ ይባላል፡፡ ይህም በሥላሴ አርአያ የተፈጠረውን ሰው ሁሉ መውደድና ማፍቀር ነው፡፡ ይህም ኀጥእ ጻድቅ፣ አማኒ መናፍቅ፣ ዘመድ ባዕድ ሳይሉና ሳይለዩ ሁሉን አስተካክሎ መውደድ ነው፡፡ ይህም ትእዛዝ ጠላትን እስከመውደድ በመድረስ ነው፡፡ “በሰማያት ላለው አባታችሁ ልጆች ትሆኑ ዘንድ ጠላቶቻችሁን ውደዱ የሚረግሟችሁን መርቁ፣ ለሚጠሏችሁ መልካም አድርጉ ስለሚያሳድዷችሁ ጸልዩ፡፡” ማቴ.5፥44

 

በአጠቃላይ ክርስቲያን ከአለባበሱ ጀምሮ ውጫዊ አቋሙም ሆነ አጠቃላይ ሕይወቱ በማናቸውም ጊዜና ቦታ ሁሉ ክርስቲያንነቱን ሊገልጡ ይገባቸዋል፡፡ ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር ኖረው ለሰውም ብርሃን ሆኖ እግዚአብሔርንና የእግዚአብሔር የሆኑትን አስደሰተ የሚባለው ያን ጊዜ ነው፡፡ እንግዲህ ክርስቲያን በምድር ሲኖር በግል ሕይወቱም ሆነ በማኅበራዊ ኑሮው ምን መምሰል እንዳለበት ራሱን ከላይ በተገለጸው በሦስቱ ሕግጋት አንጻር እየመረመረ መጓዝ አለበት፡፡ በግል ሕይወቱ ዘወትር ንስሓ እየገባ ቅዱስ ቁርባን በመቀበል እየጾመ፣ እየጸለየ፣ እየመጸወተ ሰማያዊ መንግሥትን ተስፋ በማድረግ ይጓዛል፡፡ በማኅበራዊ ኑሮውም ደግሞ ሰዎችን በሐዘናቸው ጊዜ ማጽናናት፣ በደስታቸው ተካፋይ መሆን፣ ከቸገራቸው ለችግራቸው ደራሽ በመሆን እውነተኛ ፍቅሩን ሊገልጽ ያስፈልጋል፡፡ “የኢየሱስ ሕይወት ደግሞ በሥጋችን ይገለጥ ዘንድ ሁል ጊዜ የኢየሱስን መሞት በሥጋችን ተሸክመን እንዞራለን፡፡” 2ቆሮ.4፥10

debr 10

ደብረሊባኖስ ገዳምን የሚታደጉ ሰፋፊ ፕሮጀክቶችን ተግባራዊ ለማድረግ ሰፊ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑ ተገለጸ

ኅዳር 10 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ማለደ ዋስይሁን

 

debr 10

የደብረ ሊባኖስ ገዳምን በሁለንተናዊ መልኩ ለማሳደግ የሚያስችሉ ፕሮጀክቶች ተግባራዊ ለማድረግ እየተንቀሳቀሱ መሆኑን የገዳሙ ጸባቴ አባ ኃይለ መስቀል ውቤ አስታወቁ፡፡ ኅዳር 9 2005 ዓ.ም በማኅበረ ቅዱሳን ጽሕፈት ቤት ከገዳሙ ወዳጆች ጋር በተደረገው የምክክር መርሐ ግብር ላይ ይፋ እንደተደረገው ገዳሙ ያሉበትን ችግሮች ቀርፎ በቀጣይም አርአያ ምሳሌ ወደሚሆንበት ደረጃ የሚያደርሱትን እንቅስቃሴዎች ከማኅበረ ቅዱሳን ባለሙያዎች ጋር በመተባበር ለማከናወን መታቀዱን ጸባቴው ገልጸዋል፡፡

 

በዕለቱ በምክክር መርሐ ግብሩ የተገኙት፣ ገዳሙ የሚገኝበት ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ ገዳሙ በሁሉም ወገኖች ትኩረት ተነፍጎት የቆየ መሆኑን አውስተው በሀገሪቱ ታሪክ ውስጥ ከነበረው ዘርፈ ብዙ ሚናና ከታዋቂነቱ አንጻር ጠያቂ ተቆርቋሪ አጥቶ መኖሩ ሲያሳዝናቸው መቆየቱን አውስተዋል፡፡ በዕለቱም የማኅበረ ቅዱሳን ባለሙያዎች ገዳሙ አሁን ያለበትን ወቅታዊ ሁኔታ የሚያመለክት ጥናት በተለያዩ የመረጃ ማግኛ ዘዴዎች ተጠቅመው መሥራታቸው የተገለጸ ሲሆን የጥናቱም ውጤት ጠቅለል ብሎ በኢንጂነር ዮናስ ምናሉ እና በዶክተር ሳሙኤል ኃይለማርያም ቀርቧል፡፡

 

ወቅታዊ ሁኔታውን በማሳየት ሳያበቃም ወደፊት ተግባራዊ ለማድረግ ስለታሰቡት ፕሮጀክቶች ሰፊ ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡ ወደፊትም እያንዳንዱ ፕሮጀክት የሚጠይቀውን የገንዘብ፣ የሙያ፣ የሰው ኃይል ወዘተ ፍላጎት ባመላከተ ሁኔታ ተዘጋጅቶ እንደሚቀርብ የተገለጸ ሲሆን ሁሉም በምክክሩ ላይ የተሳተፉ የገዳሙ ወዳጆች ተግባሩ በመላው ሀገሪቱ ያሉ ምእመናንን ያሳተፈ ሆኖ በጥብቅና በጥልቅ ሁኔታ  መጀመር አለባቸው ሲሉ አሳስበዋል፡፡

 

በዕለቱ በተደረገውም ውይይት ተሳታፊዎች በገዳሙ ብዙ ፕሮጀክቶች ሲተገበሩ የገዳሙ አንገብጋቢ ችግሮች ቅድሚያ እንዲሰጣቸውና በየደረጃውም የገዳሙን ልዕልና የሚያስጠብቁና ምሳሌ የሚያደርጉትን ሌሎች ላቅ ያሉ ፕሮጀክቶች ወደመተግበር እንዲገባ ሲያሳስቡ ተስተውሏል፡፡ ይህንኑ በጎ ዓላማ ከግብ ለማድረስ የሚያነሣሣ የሕዝብ ጉባኤና የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር በታኅሣሥ 14 2005 ዓ.ም በዕለተ እሑድ ከጠዋቱ 3 ሰዓት ጀምሮ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ለማከናወን ዝግጅት እየተደረገ ነው፡፡ በጥሪው የሚሳተፉና በቅስቀሳውም የሚሰማሩ እጅግ በርካታ ወገኖች የሚጠበቁ ሲሆን ይህ የመጀመሪያው መርሐ ግብር እንደሆነም ተገልጿል፡፡