001

የደቡብ ክፍለ ከተማ ሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ጉባኤ ተካሄደ

ግንቦት 2/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኩኖአምላክ

001በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የደቡብ ክ/ከተማ ሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ዓመታዊ ጉባኤውን ሚያዚያ 23 ቀን 2004 ዓ.ም. አካሂዷል፡፡ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የመሰብሰቢያ አዳራሽ በተከናወነው በዚሁ መንፈሳዊ መርሐ ግብር ላይ፡- በክፍለ ከተማው የሚገኙ 32 ሰንበት ትምህርት ቤቶች ተሳታፊ ሆነዋል፡፡ በጉባኤው ላይ ተገኝተው ትምህርተ ወንጌል የሰጡት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ ክቡር ቆሞስ መልአከ ጽዮን አባ ኅሩይ ወንድይፍራው ናቸው፡፡

የመምሪያ ሓላፊው “ልጄ ሆይ ሰው ሁን” በሚል ርዕስ ባስተማሩት ትምህርት ላይ “ የሰንበት ትምህርት ቤቶች የአንድነት ጉባኤ በየዓመቱ ሊደረግ ይገባዋል፡፡ ይህንን ጉባኤ ማካሄዳችን በየሰንበት ትምህርት ቤቶቻችን ያሉብንን ችግሮች ለማስወገድና በቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ የልማት እንቅስቃሴ የበኩላችንን እገዛ ልናደርግ እድል ይፈጥርልናል፡፡ በየሰንበት ት/ቤቱ የሚገኙ ልጆቻችንም ከቅዱስ ፓትርያርኩና ከብፁአን አባቶቻችን ቡራኬና ትምህርት የሚቀበሉበት መርሐ ግብር ይሆናል በአጠቃላይም ይህን ጉብኤ ለማዘጋጀት የማደራጃ መምሪያው ድጋፍ አይለየውም” ብለዋል፡፡

 

የክፍለ ከተማው ሰንበት ትምህርት ቤቶች ምክትል ሰብሳቢ የሆነው ወጣት ዘሪሁን መኮንን በጉባኤው ላይ ባቀረበው ሪፖርት ሰንበት002 ትምህርት ቤቶቻችን በየዓመቱ የደመራ በዓልን ለማክበር በአደባባይ ከመሰባሰብ ውጪ መንፈሳዊ አንድነት ፈጥረው እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነት ሊያበረክቱት የሚገባቸውን ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከት ሳይቻላቸው በርካታ ጊዜያት ማለፋቸውን አስታውሶ ከአምስት ዓመታት ወዲህ ግን የተጠናከረና ሰንበት ትምህርት ቤቶችን በእኩል ሊያሳትፍ የሚችል መተዳደሪያ ደንብ መዘጋጀቱን አስታውቋል፡፡

 

ከዚህ በተጨማሪ በክፍለ ከተማው የሚገኙ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ኅብረታቸውን በመጠበቅ የጋራ ዕቅዳቸውን ለማሳካት አገልግሎታቸውን አጠናክረው መቀጠላቸውን ገልጿአል፡፡ ም/ሰብሳቢው በክፍለ ከተማው የተሠሩ ሥራዎችን ሳያብራራ፡- በሁሉም ሰንበት ትምህርት ቤቶች ያሬዳዊ ዝማሬን ለማስጠናት የሚችሉ የአሰልጣኞች ሥልጠና ለሦስት ዓመታት ተካሂዷል” ብሏል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ መምህራንን በማፍራቱና በማሰልጠን ረገድ በ3 ጊዜያት ቁጥራቸው ከ146 በላይ አባላትን ማስተማሩንና በተመሳሳይ መልኩ ከልዩ ልዩ አድባራት የተውጣጡ መምህራን የሰጡትን የአብነት ትምህርት በሚገባ የተከተሉ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት ሥልጣነ-ክህነት እንዲቀበሉ ማድረጉን አስረድቷል፡፡ የአዲስ አበባ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን አንድነት ለመመሥረት የበኩሉን አስተዋጽኦ በማበርከት ላይ የሚገኘው ክፍለ ከተማው የተሃድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴን የመከታተል ቤተ ክርስቲያንን የመጠበቅ፣ እንዲሁም ለሰንበት ትምህርት ቤቶች የአስተዳደርና ሒሳብ አያያዝ ሥልጠና መስጠቱን ገልጿል፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይ “ድንግል ሆይ ብረሳሽ” የተሰኘ መነባንብ፣ እንዲሁም “ሰንበት ት/ቤት” የሚል ግጥም ቀርቧል፡፡

 

ከጉባኤው በኋላ የክፍለ ከተማው ሰንበት ትምህርት ቤቶች ሰብሳቢ የሆነው ወጣት ሳሙኤል እሸቴን “የደቡብ ክፍለ ከተማ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማኅበር አወቃቀሩ ምን ይመስላል?” ስንል ላቀረብንለት ጥያቄ ምላሽ ሲጠጥ “….በሥራ አስፈፃሚ ደረጃ የተዋቀረ ተጠሪነቱም ለአዲስ አበባ ሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት የሆነ የአገልግሎት ክፍል አለ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ዘጠኝ የአገልግሎት ክፍሎች አሉ፡፡ እነኚህን ለማገዝ በክፍለ ከተማችን የሚገኙ 32 ሰንበት ትምህርት ቤቶችን በ4 ምድብ በመክፈል እየተናበቡ ተግባራትን እንዲያስፈጽሙ እያደረግን እንገኛለን፡፡ ይህንንም ለማገዝ በማደራጃ መምሪያው መልካም ፈቃድና እገዛ በመካነ ሰማዕት ቅዱስ ቂርቆስ ቤተ ክርስቲያን አንድ ቢሮ ተሰጥቶናል” ብሎናል፡፡

 

003ወጣት ሳሙኤል ከዚሁ ጋር አያይዞ ሚያዝያ 23 ቀን 2004 ዓ.ም. ስለተከናወነው መርሐ ግብር በተመለከተ ሲናገር “የሰንበት ትምህርት ቤቶች ቀን በሚል ርእስ በየዓመቱ የሚከናወነው መርሐ ግብር ዘንድሮ ለ4ኛ ጊዜ የተከናወነ ነው፡፡ ሰንበት ትምህርት ቤቶች በአንድነት በአንድ ጉባኤ ተሰብስበው የመማራቸው ፋይዳው፡-

 

የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት ለእናት ቤተ ክርስቲያን ሊያበረክቱ የሚገባቸውን አስተዋጽኦ እንዲያስቡ ያደርጋቸዋል፤ በቅርቡም በዝቋላ የአቡነ ገ/መንፈስ ቅዱስ ገዳም ላይ የደረሰውን ቃጠሎ ለማጥፋት እርስ በርስ ተጠራርተው መሄዳቸውና ያንን የመሰለ አስደናቂ ተግባር ፈጽመው መመለሳቸው የመገናኘቱ ውጤት ነው፡፡ በሌላ በኩል የማደራጃ መምሪያችን ሓላፊ ቆሞስ አባ ኅሩይ ወንድ ይፍራው በጉባኤያችን ላይ ተገኝተው በየክፍለ ከተማው የሚገኙ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ቢያንስ  በዓመት ሁለት ጊዜ ትምህርትና ቡራኬን ከብፁዓን አባቶች መቀበል እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡ በሰላሳ ሁለቱ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ምን ያህል አባላት አሉ? የሚል ጥያቄ ያቀረብንለት ወጣት ሳሙኤል “በግምት ከ20 እስከ 30ሺ የሚደርሱ አባላት አሉን፡፡ በቅርቡ ግን በእያንዳንዱ ሰንበት ትምህርት ቤት ምን ያህል አባላት እንደሚገኙ በዕድሜአቸው በትምህርታቸው /በሙያቸው/ እንዲሁም በሌላ አስፈላጊ መረጃዎች የተጠናከረ መረጃ /ዳታ/ የማሰባሰብ ሥራ እንጀምራለን፡፡ ይህም ከፍተኛ ጥቅም አለው፡፡ ምክንያቱም ቤተ ክርስቲያን ምን ያህል ያልተነካ የሰው ኃይል በሰንበት ትምህርት ቤቶቿ እንዳላት መረጃ ይሰጣልና፡፡”

 

በስተመጨረሻ የደቡብ ክፍለ ከተማ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን በመወከል ማስተላለፍ የምትፈልገው ነገር ካለህ? ተብሎ የተጠየቀው ወጣት ሳሙኤል፡፡

 

“የሰንበት ትምህርት ቤቶቻችን በአብነት ትምህርት ላይ ትኩረት አድርገው መሥራት ይጠበቅባቸዋል፡፡ የአብነት ትምህርት ጉዳይ ለነገ የሚባል ሳይሆን ቅድሚያ የሚሰጠው ነገር ነው፡፡ ሰንበት ትምህርት ቤቶች የነገ የሀገርና የቤተ ክርስቲያን ተረካቢ ትውልድ የሚፈሩባቸው ከመሆናቸው አንፃር በትክክል የቤተ ክርስቲያኒቱ ትምህርት ሊሰጥባቸው ይገባል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በተናጠል ከመሥራት ወጥተን /የአንዲት ርትዕት ቅድስት ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን ልጆች በመሆናችን/ በአንድነት የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ለማፋጠን መሥራት ይኖርብናል፡፡ በመጨረሻ በሰንበት ትምህርት ቤቶች የምንገኝ ወጣቶች ሁላችን ሀገራዊ ራእይ ሃይማኖታዊ አቋምን አጠናክረን ልንይዝ ይገባናል” ብሏል፡፡

lidetaleMariam 1

“መሠረታቲሃ ውስተ አድባር ቅዱሳን፡- መሠረቶቿ የተቀደሱ ተራሮች ናቸው” /መዝ.86፥1/


በዲ/ን ዮሴፍ ይኩኖአምላክ

lidetaleMariam 1ይህ ቃል የእመቤታችንን አያቶቿን የቀደሙ ወላጆቿን ንጽሕና፣ ቅድስና፣ ክብር አስመልክቶ ቅዱስ ዳዊት የተናገረው የምስክርነት ቃል ነው፡፡ ይህ ምስክርነት አካላዊ ቃል እግዚአብሔር ወልድ ለኩነተ ሥጋ የመረጣት ቅድስት ድንግል ማርያም ወላጆቿ ንጹሐን፣ ቅዱሳን መሆናቸውን ያስረዳል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም ሲመላለስ፡- “መልካም ዛፍ ሁሉ መልካም ፍሬን ያፈራል፤ ክፉ ዛፍም ክፉ ፍሬን ያፈራል፡፡ መልካምም ዛፍ ክፉ ፍሬን ማፍራት፥ ክፉ ዛፍም መልካም ፍሬን ማፍራት አይችልም” ማቴ.7፥17-18፡፡ በማለት እንደተናገረው እመቤታችን ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም የተገኘችባቸው ወላጆቿ ሁሉ ቅዱሳን ንጹሐን፣ እግዚአብሔርን የሚወዱና የሚያከብሩ መሆናቸውን ልብ ይሏል፡፡ ለመሆኑ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የዘር ሐረግና የትውልድ ታሪኳ ምን ይመስላል?

 

በነገረ ማርያም ሰፍሮ ከምናገኘው ሰፊ ታሪክ ከፊሉን እንዲህ አቅርበነዋል፡፡ መልካም ንባብ!

የእመቤታችን ቅድመ አያቶቿ ቴክታ በጥሪቃ ይባላሉ፤ ይህ ቀራቸው የማይባሉ ባለጸጎች ነበሩ፤ ብዕላቸውም የወርቅ፣ የብር፣ የፈረስ፣ የበቅሎ፣ የሴት ባሪያ፣ የወንድ ባሪያ ነው፡፡ ከወርቁ ብዛት የተነሣ እንደ አምባር እንደ ቀለበት እያሠሩ፤ ከበሬው ከላሙ ቀንድ ያደርጉት ነበር፡፡ ይህን ያህል አቅርንተ ወርቅ፤ ይህን ያህል አቃርንተ ብሩር ተብሎ ይቈጠር ነበር እንጂ፤ የቀረው አይቈጠርም ነበር፡፡ ከዕለታት ባንደኛው በጥሪቃ ከቤተ መዛግብት ገብቶ የገንዘቡን ብዛት አይቶ፤ “ቴከታ እኔ መካን፤ አንቺ መካን ይህ ሁሉ ገንዘብ ለማን ይሆናል?” አላት “እግዚአብሔር እንጂ ከኔ ባይሰጥህ ወይ ከሌላ ይሰጥህ ይሆናል፤ አግብተህ አትወልድምን?” አለችው፡፡ “ይህንስ እንዳላደርገው አምላከ እስራኤል ያውቃል” አላት፤ በዚህ ጊዜ አዘኑ፤ ወዲያው ራእይ አይተዋል፤ ነጭ እንቦሳ ከበረታቸው ስታወጣ፣ እንቦሳይቱ እንቦሳ እየወለደች እስከ ስድስት ስታደርስ ስድስተኛይቱ ጨረቃን፣ ጨረቃ ፀሐይን ስትወልድ አይተው፥ በሀገራቸው መፈክረ ሕልም /ሕልም ተርጓሚ/ አለና ሂደው ነገሩት፤ “ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ፤ ጨረቃይቱ ከፍጡራን በላይ የምትሆን ልጅ ትወልዳላችሁ የፀሐይ ነገር ግን አልተገለጸልኝም እንደ ነቢይ እንደ ንጉሥ ያለ ይሆናል” አላቸው፡፡ እነርሱም “ጊዜ ይተርጉመው” ብለውት ሄዱ፡፡ ከዚህ በኋላ ፀነሰች፤ ወለደች ስሟን ሄኤማን አለቻት፤ ሄኤማን ማለት ረካብኩ ስእለትየ ረከብኩ ተምኔትየ /የፈለግሁትን የለመንኩትን አገኘሁ/ ማለት ነው፡፡ ሄኤሜን ዴርዴን፤ ዴርዴ ቶናን፣ ቶና ሲካርን፣ ሲካር ሄርሜላን፣ ሄርሜላ ሐናን ወለደች፡፡ ሐና አካለ መጠን ስትደርስ ከቤተ ይሁዳ ለተወለደ ኢያቄም ለሚባል ደግ ሰው አጋቧት፣ ምክነት ወርዶ እንደ አያቶቿ ሆናለች፤ ብዕሉ ግን በመጠን ሆኗል፡፡

 

ከጎረቤቷ በዝሙት የምትኖር አንዲት ሴት ነበረች፡፡ ሐና “ዛሬ ቤተ ክርስቲያን እስማለሁ ብዬ ነበር፤ ነገር ግን የምለብሰው ልብስ የለኝም” አለቻት፡፡ እርሷም “ልብስማ የኔ ካንድ ሁለት ሦስት ልብስ አለልሽ አይደለም? ያንን ለብሰሽ አትሄጅምን?” አለቻት፡፡ “ያንቺ ልብስ የተሰበሰበ በዐስበ ደነስ በዐስበ ዝሙት ነው፡፡ እግዚአብሔር ንጹሐ ባሕርይ ነውና ንጹሕ ነገር ይወዳል፤ ይህን ለብሼ ብለምነው ምን ይሰማኛል ብዬ ነዋ” አለቻት፡፡ “ሐና፤ እኔ በምን ምክንያት ልጅ ነሣት እያልሁ ሳዝንልሽ እኖር ነበር፤ ለካ እንደ ድንጊያ አድርቆ ያስቀረሽ ይህ ክፋትሽ ነው” አለቻት በዚህ አዝናለች፡፡

 

በሌላ ጊዜም ሐናና ኢያቄም “መሥዋዕት እናቀርባለን” ብለው ከቤተ መቅደስ ሄዱ፤ ሊቀ ካህናቱ ሮቤል ይባል ነበር፡፡ “ወኢይተወከፍ መሥዋዕቶሙ ለመካናት እንጂ ይላል፤ “እናንተማ ብዝኁ ወተባዝኀ… ብሎ ለአዳም የነገረውን ያስቀረባችሁ ርጉማን አይደላችሁምን? ቢጠላችሁ ነው እንጂ ቢወዳችሁማ ልጅ ይሰጣችሁ አልነበረምን? መሥዋዕታችሁን አልቀበልም” ብሏቸው በዚህ እያዘኑ ተመልሰዋል፡፡ …. ከዛፍ ሥር ተቀምጠው አርጋብ /ርግቦች/ ከልጆቻቸው ጋራ ሲጫወቱ ዕፅዋት አብበው አፍርተው አይታ “አርጋብን በባሕርያቸው እንዲራቡ፣ ዕፅዋትን እንዲያብቡ እንዲያፈሩ የምታደርግ የኔ ተፈጥሮዬ ከድንጋይ ይሆን ልጅ የነሣኸኝ” ብላ አዘነች፡፡ ከቤታቸው ሂደው “ወንድ ልጅ ብንወልድ ወጥቶ ወርዶ አርሶ ቆፍሮ ይርዳን አንልም ለቤተ እግዚአብሔር አንጣፊ፤ ጋራጅ ሆኖ ይኖራል፤ ሴት ብንወልድ ዕንጨት ሰብራ ውኃ ቀድታ ትርዳን አንልም፤ ለቤተ እግዚአብሔር መሶበ ወርቅ ሰፍታ መጋረጃ ፈትላ ትኑር” ብለው ብፅዓት ገብተዋል፡፡

 

የሐምሌ  30 ዕለት እሷ ለሱ “ፀምር ሲያስታጥቁህ መቋሚያህ አፍርታ ፍጥረት ሁሉ ሲመገባት አየሁ” ብላ፤ እሱ ለሷዋ “ጻዕዳ ርግብ ሰባቱን ሰማያት ሰንጥቃ መጥታ በራስሽ ላይ ስታርፍ፤ በቀኝ ጆሮሽ ገብታ በማኅፀንሽ ስታድር አየሁ” ብሎ ያዩትን ራእይ ተጨዋውተዋል፡፡ በሀገራቸው መፈክረ ሕልም አለና ሂደው ነገሩት፡፡ “ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ” አላቸው፡፡ “አንተስ አልፈታኸውም ጊዜ ይፍታው” ብለው ተመልሰዋል፡፡ በነሐሴ 7 ቀን መልአክ መጥቶ ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ ብሏቸው በብሥራተ መልአክ በፈቃደ አምላክ እመቤታችን ተፀነሰች፡፡ በተፀነሰችም ጊዜ ብዙ ተአምራት ተደርጓል፡፡

 

በርሴባ የምትባል አክስት ነበረቻት አንድ ዐይና ነች፤ “ሐና እግዚአብሔር በረድኤት ጎበኘሽ መሰለኝ” ብላ ማኅፀኑዋን ደሳ ዐይኗን ብታሸው በርቶላታል፡፡ ይህን አብነት አድርገው ሕሙማን ሁሉ ማኅፀኑዋን እየዳሰሱ የሚፈወሱ ሆነዋል፡፡ ዳግመኛም ሳምናስ የሚባል ያጎቷ ልጅ ነበር ሞተ፤ ትወደው ነበርና ያልጋውን ሸንኮር ይዛ እየዞረች ስታለቅስ ጥላዋ ቢያርፍበት “ሰላም ለኪ ኦ እምሔውቱ ለዘገብረ ሰማየ ወምድረ” ብሎ ከመፈክረ ሕልም የቀረውን ተርጉሞላታል፡፡

 

ከዚህ በኋላ አይሁድ ለምቀኝነት አያርፉምና “ቀድሞ ከነዚህ ወገን የሚሆኑ ዳዊት ሰሎሞን አርባ አርባ ዘመን እንደሰም አቅልጠው እንደ ገል ቀጥቅጠው ገዙን፡፡ አሁን ደግሞ ከዚህች የተወለደ እንደምን ያደርገን ይሆን?” ብለው በጠላትነት ተነሡባቸው፤ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ለኢያቄም “አድባረ ሊባኖስ ይዘሃት ሂድ” ብሎት እመቤታችን በሊባኖስ ተራራ ተወልዳለች፡፡ ይህም አስቀድሞ እግዚአብሔር ባወቀ “እምሊባኖስ ትወፅእ መርዓት … ሙሽራ /እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም/ ከሊባኖስ ትወጣለች” በማለት ጠቢቡ የተናገረው ቃለ ትንቢት ነው፡፡ /መኃ.4፥8/

 

ዮም ፍሥሐ ኮነ በእንተ ልደታ ለማርያም፤ በእመቤታችን ልደት ምክንያት ዛሬ ደስታ ሆነ፡፡

በግንቦት 1 ቀን /5ሺ ከ5መቶ የመከራው ዘመን ሊያልቅ 15 ዓመታት ሲቀሩት/  ሊባኖስ በሚባል ተራራ ከፀሐይ የምታበራ ሴት ልጅ ተወለደች፡፡ ይህቺውም ፍጥረት ሁሉ /ደቂቀ አዳም ሁላቸው/ ተስፋ ሲያደርጓትና ሲጠባበቋት የነበረች የድኅነታቸው ምልክት እመቤታችን ናት፡፡

 

ሶሪያዊው ሊቅ ቅዱስ ኤፍሬምም “አክሊለ ምክሕነ ወቀዳሚተ መድኀኒትነ፡፡ ወመሠረተ ንጽሕነ ኮነ በማርያም ድንግል፡- የመመኪያችን ዘውድ የደኅንነታችን መጀመሪያ የንጽሕናችንም መሠረት በድንግል ማርያም ሆነልን” በማለት መናገሩ ስለዚህ ነው፡፡

 

  • አክሊል ምክሐነ፡- አላት ይህም አክሊል የወዲህኛው፣ ምክሕ የወዲያኛው ነው፡፡ ከነገሥታት መካከል እንደ ዳዊት የከበረ የለም፡፡ ምንም እንኳን ቅዱስ ዳዊት የከበረ ቢሆን የመመኪያችንን ዘውድ ማምጣት አልተቻለውም፡፡
  • ወቀዳሚተ መድኀኒተ አላት፡- ቀዳሚተ የወዲህኛው መድኀኒት የወዲያኛው ነው፡፡ ከመሳፍንት ወገን የሚሆን ኢያሱ ምንም የስሙ ትርጓሜ መድኃኒት ቢሆን የደኅንነታችን መጀመሪያ መሆን አልተቻለውም፡፡
  • ወመሠረተ ንጽሕና አላት፡- መሠረት የወዲህኛው፤ ንጽሕ የወዲያኛው ከነቢያተ እግዚአብሔር ወገን የሚሆን ኤልያስ በድንግልና በንጽሕና መኖሩ የሚታወቅ ነው፡፡ ነገር ግን ምንም ንጹሕ ድንግል ቢባል የንጽሕናችን መሠረት መሆን አልተቻለውም፡፡ የመመኪያችን ዘውድ፣ የደኅንነታችን መጀመሪያ፤ የንጽሕናችን መሠረት ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፤” በማለት ተናግሯል፡፡ በእርሷ ምክንያትነት መድኀኒዓለም የሚፈጽምልንን ካሳ ነቢያትና የቀደሙ አበው ሁሉ የእርሷን መወለድ በናፍቆት ሲጠባበቁ ነበር፡፡ ከነቢያት አንዱ የሆነ ኢሳይያስም “የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ዘርን ባያስቀርልን ኖሮ እንደ ሰዶም በሆንነ እንደ ጎሞራም በመሰልነ ነበር፡፡” በማለት መናገሩ በእርሷ መገኘት ከጥፋት መዳናችንን ሲገልጽ ነው፡፡ ኢሳ.1፥9

ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እንደ ተወለደች የሐና ዘመዶቿና ጎረቤቶቿ በሰሙ ጊዜ ፍጹም ደስ ብሏቸው ወደ ሊባኖስ ተራራ ተሰበሰቡ፡፡ ሕፃኗን /እመቤታችንን/ ተመልክተው ፍጹም አደነቁ፡፡ እርስ በርሳቸውም እንደዚች ያለች ብላቴና ከቶ አየተን አናውቅም ተባባሉ፤ ጸጋ እግዚአብሔር በርሷ አድሯልና፤ የእግዚአብሔርም ብርሃን በሰውነቷ ሁሉ መልቷልና፡፡

 

ከኢያቄምና ከሚስቱ ከሐና ጋራ ደስ እያላቸው የእግዚአብሔርን ቸርነት እየተናገሩ ሰባት ቀን ተቀመጡ፤ ያችንም ብላቴና ስምዋን ማርያም አሏት ይኸውም የእግዚአብሔር ስጦታ ማለት ነው፡፡ ሰባቱንም ቀን በፈጸሙ ጊዜ በፍቅር ወደ ቤታቸው ገቡ፡፡

 

በዚህ ትውፊት መሠረት ኢትዮጵያውያን ምእመናን በየዓመቱ ግንቦት 1 ቀን የእመቤታችንን ልደት ከቤታቸው ወጥተውና ከያሉበት ተሰባስበው ንፍሮ ቀቅለው፣ አነባብሮ ጋግረውና ሌላም እንደ አቅማቸው /ዝክር አዘጋጅተው/ በመንፈሳዊ ደስታ ዛሬም ድረስ ያከብሩታል፡፡

 

የእመቤታችን ስሞችና ትርጓሜያቸው፡፡

ማርያም ማለት ፍጽምት ማለት ነው፡፡ ለጊዜው መልክ ከደምግባት አስተባብራ ተገኝታለችና፡፡ ፍጻሜው ግን ንጽሐ ሥጋ ከንጽሐ ነፍስ ድንጋሌ ሥጋ ከድንጋሌ ነፍስ አስተባብራ ተገኝታለችና፡፡ አንድም ማርያም ጸጋ ወሀብት ማለት ነው፡፡ ለጊዜው ለእናት ለአባቷ ጸጋ ሆና ተሰጥታለች፡፡ ፍጻሜው ግን ለሰው ሁሉ ጸጋ ሁና ተሰጥታናለችና፡፡

 

አንድም፡- ማርያም ማለት መርሕ ለመንግሥተ ሰማያት ማለት ነው፡፡ ምእመናንን መርታ ገነት መንግሥተ ሰማያት አግብታለችና፡፡ አንድም ማርያም ማለት ልዕልት ማለት ነው፡፡ ከፈጣሪ በታች ከፍጡራን ሁሉ በላይ ናትና አንድም ማሪሃም ማለት እግዝእተ ብዙኀን ማለት ነው አብርሃም ማለት አበ ብዙሃን እንደሆነ ማለት ነው፡፡

 

እንግዲህ ለነቢያተ ዜና ትንቢታቸው ለሐዋርያት ስብከታቸው ለክርስቲያኖች ሁሉ ተስፋቸው የሆነች እመቤታችን የተወለደችበትን ቀን ሁላችን ምእመናን በፍጹም ፍቅርና ደስታ እናከብረዋለን፡፡

 

ፈጣሪያችን ልዑል እግዚአብሔር ለተዋሕዶ ከመረጣት ከዓለመ አንስት ተለይታ በንጽሕና በቅድስና አጊጣ የመመኪያችን ዘውድ ከሆነች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በረከት ረድኤት ይክፈለን፡፡ አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የቀኝ ዐይን – ድንግል ማርያም

በዲ/ን ብርሃኑ አድማስ

አፍጣኒተ ረድኤት ማርያም በጊዜ  ምንዳቤ ወአጸባ ለዐይን እምቀራንባ፤ አንቲ ውእቱ ረዳኢተ ያዕቆብ በቤተ ላባ፤ በኩሉ ኅሊናሃ ወበኩሉ አልባባ፤ዘኢታፈቅረኪ ነፍስ ትሠሮ እምሕዝባ፡፡

 የነገረ ማርያም ሊቅ(Marian Doctor)እየተባለ የሚጠራው ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ እመቤታችንን በብዙ ምሳሌ እየመሰለ፣ እየተረጎመና እያመሰጠረ ብዙ ጊዜ አመስግኗታል፡፡ ምንም እንኳን እኛ የምናውቀው የምስጋና ድርሰቱ ለጸሎት የምንጠቀምበት ውዳሴ ማርያም ቢሆንም ከትርጓሜና ከስብከቶቹ ውጪ ከሦስት ሚሊዮን በላይ ስንኝ ያላቸው የምስጋና ድርሰቶችን(Hymns) መድረሱን ታሪክ ጸሐፊው ሶዝመን መዝግቦልናል፡፡ ከነዚህ የምስጋና ድርሰቶቹ መካከልም ‹‹በእንተ ልደት››(On Nativity) እና ‹‹በእንተ ቤተ ክርስቲያን››(On the Church)በተባሉ ትልልቅ ድርሰቶቹም እመቤታችንን ደጋግሞ ያመሰግናታል፡፡

በተጠቀሱት ሁለቱም ድርሰቶቹ እመቤታችንን ለማመስገን ከተጠቀመባቸው ምሳሌዎች ውስጥ አንዱ “ዐይን” ነው፡፡ ሊቁ ስለ ቤተክርስቲያን በደረሰው የምስጋና መዝሙሩ ውስጥ እንዲህ ይላታል፤ ‹‹ዐይን ጥርት የሚለው ከፀሐይ ብርሃን ጋር ተዋሕዶ ከብርታቷ ኃይልን ከውበቷም ነጸብራቅን ሲቀበል ነው፤ በዚህ ጊዜ በግለቷ ይሰነገላል፣ያበራል፤ በውበቷም ያጌጣል፤… ልክ እንደዚሁ ማርያም ዐይን ናት፤ብርሃን (ጌታ) ማደሪያውን በእርሷ አዘጋጀና መንፈሷን ጽሩይ አደረገ፤አሳቦቿን አጠራ፣ኅሊናዋንም ንጹሕ አደረገ፤የድንግልናዋንም ክብር አበራው ››/Hymns on the Church, 36, 1-2/፡፡ ሊቁ በዚሁ ድርሰቱ ውስጥ ሌላ ቦታ ላይ ደግሞ፤ ‹ለዚህ ዓለም ሁለት ዐይኖች ተሰጡት፤ ማየት ያልተቻላት የግራ ዐይን ሔዋን ስትሆን፣ የምታበራው የቀኝ ዐይን ደግሞ (እመቤታችን) ማርያም ናት፡፡በማታየው በጨለማዋ ዐይን ምክንያት መላው ዓለም ጨለመ፤ ስለዚህም ሰዎች በጨለማ ጥላ ውስጥ ሆነው ሲዳብሱ ያገኙት ሁሉ አምላክ ፣ ሐሰቱም እውነት መሰላቸው፡፡ነገር ግን ዓለም እንደገና በሌላ ዐይኑ ባበራና (ባየና) ሰማያዊው ብርሃንም በዚች ዐይን ሰሌዳ ውስጥ ባንጸባረቀ ጊዜ ሰዎችም ቀድሞ ያገኙትን(ያመለኩትን) የኑሮአቸው ውድቀት(የባሕርያቸው መጎስቆል) መሆኑን ተረድተው ወደ ማንነታቸው ተመለሱ (አንድነታቸውን አገኙ)›› ይላል /Ibid, 37, 5-7/::

 

በዚህ መሠረት የእመቤታችን ልደት ዓለም ማየት የጀመረበት ዕለት ነው ማለት ነው፡፡ በርግጥም በነገረ ማርያም መጽሐፋችን ላይ እንደተገለጸው እመቤታችን በቴክታና በጥሪቃ(ሰባተኛ ቅድመ አያቶቿ) በታየው ሕልም መሠረት ዓለምን ሰፍኖበት ከነበረው ድቅድቅ የኃጢኣት ጨለማ እፎይታ የሰጠችው ጨረቃ እርሷ ናት፡፡ በጨለማ ሲያዩት የሚያስፈራውና ሌላ ሌላ የሚመስለው ጉቶው፣ ቁጥቋጦው ፣ ድንጋዩ ፣ ጉብታው….ሁሉ ተራ ነገር መሆኑ የተጋለጠባት፤ ሰዎችም የሰገዱለት ሁሉ አምላክና ጌታ መሆኑ ቀርቶ ድንጋይ ጉብታ መሆኑን ማየት የጀመሩባት፣ ከደገኛው ፀሐይ ክርስቶስ መውጣት በፊት ከረጂሙ ዘመን ጨለማ ጭንቀት የተገላገልንባት ጨረቃ፣ ብርሂት የቀኝ ዐይን እመቤታችን ማርያም ናት፡፡ ስለዚህም ልደቷን የጨለማችን መገፈፍ፣ የዐይናችን ማየት፣ የብርሃናችንም መውጣት ነውና በፍጹም ደስታ እናስበዋለን፤ እናከብረዋለንም፡፡

 

ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬምን የምናስታውሰውም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ብዙ በማመስገኑ ብቻ ሳይሆን ግሩም አድርጎ በማመስጠሩና እንዲህ ያለ ልዩ ልዩ ነገር በማምጣቱም ጭምር ነው፡፡ ለነገሩ ሰው የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ ከሆነ በኋላ ይህን ሁሉ ማድረጉ አያስደንቅም፡፡ የሆነው ሆኖ የእርሱን ያህል በልዩ ልዩ ሕብረ-አምሳል ያመሰገናት ያለ አይመስልም፡፡ሊቁ በልደት ድርሰቱም‹‹እናትህ አስደናቂ ናት፤ ጌታ ወደ እርሷ ገባና አገልጋይ ሆነ፤ እየተናገረ ገብቶ በእርሷ ውስጥ ግን ዝም አለ፤ ወደ እርሷ በነጎድጓድ ድምፅ ገብቶ በእርሷ ውስጥ ጸጥታን አሳደገ፤ የዓለሙ እረኛ ገብቶ በግ ሆኖ ተወለደ፤ እንደ በግም ‹ባ› እያለ ተገለጠ ››/On Nativity, 11, 6/ እያለ አስደናቂነቷን እየደጋገመ ይናገርላታል፡፡አንድ ብቻ ጨምሬ ወደ በዓሉ ልመለስ ፤ቅዱሱ ሊቅ ጌታን እንዲህ ይለዋል፤ ‹‹አንተና እናትህ ብቻ ተወዳዳሪ የሌላችሁ ውቦች ናችሁ፤ በአንተ ላይ ምንም ምን ትንታ(mark) በእናትህም ላይ እንከን(stain) የለም››/Carmina Nisibena, 27,8/፡፡ምንኛ ግሩም ምስጋና፣ እንዴትስ ያለ ፍቅር፣ እንደምንስ ያለ መረዳት ነው? መብቃት ነዋ! መብቃት! ከሌላ ከምን ይገኛል? እርሱ ካልገለጸ፡፡

 

ከቅዱስ ኤፍሬም ሌሎች ድርሰቶች የተነሣሁትና ርእሴንም በእርሱ ምስጋና ያደረግሁት እንዲሁ አይደለም፡፡ በአሁኑ ጊዜ ውዳሴ ማርያም እየተጣጣለና ድርሰቱም የእርሱ ሳይሆን የኢትዮጵያውያን ነው (ምነው በሆነና ነበር) ፤ ወይም ደግሞ እርሱ ስለ ሌላ የደረሰውን የእኛ ሰዎች የማርያም ምስጋና ነው ብለው ነው እንጂ እርሱስ እንዲህ አይልም መባል ስለተጀመረ እርሱ ስለ እርሷ ከደረሰዉ ወደ ግእዝ የተተረጎመዉ ትንሽ መሆኑንና ከላይ ለምሳሌነት ካቀርብኳቸው በላይ በውዳሴ ማርያም ምን አዲስ ነገር አለ ለማለት ነው፡፡ ይህችን ታህል ጥቆማ ከሰጠሁ ቦታውም ጊዜውም የጽሑፉም ዓላማ በዚህ ጉዳይ ላይ መከራከር አይደለምና ወደ እናታችን በዓለ ልደት በረከት ላምራ፡፡

 

በርግጥም ፍጹም ልዩ

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በማይጠረጠር መልኩ ከፍጥረት ሁሉ ልዩ ናት፡፡ በድንግልና ላይ እናትነት፣ በክብረ ድንግልና ላይ ክብረ ወሊድ፣ በድንጋሌ ሥጋ ላይ ድንጋሌ ነፍስና ድንጋሌ ኅሊና የተሰጠው ከእርሷ በቀር ማንም የለም፡፡ ይህም ብቻ አይደለም፤ ምንም እንኳ ‹‹በልቧ ትጠብቀው ነበር››/ሉቃ.2፡51/ ተብሎ እንደተጻፈው አትናገረው እንጂ ከፍጥረት ወገን እንደ እመቤታችን እርሱን ለማወቅ የተቻለው ፍጥረት የለም፡፡ ሊቁ ኦሪገን በሉቃስ ወንጌል ትርጓሜው ላይ እንደገለጸው ስለ አምላክ ፍጥረት ሊያውቀው የሚቻለው የመጨረሻው የእውቀት ደረጃ ላይ የደረሰችው እመቤታችን ብቻ ናት፡፡ እንደ እርሱ ትርጓሜ እመቤታችን ፍጡር ለፈጣሪው ክብር ሊጨምርለት እንደማይቻለው እያወቀች  ‹‹ተዐብዮ ነፍስየ ለእግዚአብሔር – ነፍሴ እግዚአብሔርን ታከብረዋለች›› ያለችው ፍጡር ሊረዳው የሚቻለው የመጨረሻው ደረጃ ላይ ደርሳ በዚያ መጠን ማመሰገኗን ስትገልጽልን ነዉ ይላል፡፡በርግጥም በዚህ መጠን ከርሷ በላይ ሊደርስ የሚቻለው እንዴት ሊኖር ይችላል? ይህ የሚያመለክተውም ገና በምድር ሳለች ለፍጥረት የሚገባው ለዚህ የመጨረሻ ብቃት ከደረሰች ከዚህ ዓለም ከሔደች በኋላማ ይልቁንም እንዴት ያለውን የተወደደውንና ከፍጥረት ሁሉ የላቀውን ምስጋና ታቀርብልን ይሆን? ምን ጥርጥር አለው? ልዩ የሆነውን ልታቀርብ የሚቻላት ልዩ እናት፡፡

 

ለዚህም የበቃችው ራሷን ለሰው በሚቻለው ከፍተኛው መጠን እንደምትጠብቅ አስቀድሞ የሚያውቅ ፈጣሪ እርሱም ደግሞ ጠበቃትና ከፍጥረት ወገን ልዩ ሆነች፡፡ ቀድም ብለን የተመለከትናቸው የቅዱስ ኤፍሬም ጥቅሶች የሚያረጋግጡልንም ይህንኑ ነው፡፡ ብርሂት የሆነች ዐይን ለሰውነት መብራት የምትሆነው የፀሐይ ብርሃን ሲዋሐዳት እንደሆነው ሁሉ እርሷም በራሷ ብርሃነ ዐይን ንጽሐ ሥጋ ወኅሊና ላይ የብርሃን ጌታ ብርሃን የተባለ ጸጋዉን አሳድሮ ንጽሕናዋን ወደር የለሽ አደረገዉ፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ርብቃ ለይስሐቅ የታጨችበትን የሚናገረዉ አንቀጽ ላይ ‹‹ብላቴናይቱም መልክዋ እጅግ ያማረ፥ ወንድ የማያውቃት ድንግልም ነበረች››/ዘፍ. 24፣16/ የሚለውን ሲተረጉም ‹ወንድ የማያውቃት› የሚለውን ለሥጋ ድንግልናዋ ከሰጠ በኋላ ‹ድንግልም ነበረች› ያለው ደግሞ ለመደጋገም ሳይሆን በኅሊናዋም ያልባከነች የተጠበቀች ነበረች ሲል ነው ይላል፡፡ ይሁን እንጂ እንደዚህ ያለችው ድንግል ርብቃ ድንገት(ለርሷ) ያገኘችውና ማንነቱን እንኳ በውል የማታውቀው ሽማግሌ (የአብርሃም መልክተኛ) ቤተሰቦቿን በጠየቀው መሠረት ወላጆቿ ጠርተው ‹‹ከዚህ ሰው ጋር ትሄጃለሽን?›› ብለው በጠየቋት ጊዜ ሳታንገራግር ‹‹እሔዳለሁ›› አለች፤ መሰስ ብላም ተከተለችው፡፡/ዘፍ 24፣58/ እመቤታችን ግን የከበረ መልአክ ተገለጾ ሲያነጋግራት እንኳ የልቡናዋ በር ለወሊድ አልተንኳኳም፡፡ ለልማዱ ሴት ልጅ ‹‹ትጸንሻለሽ፣ ትወልጃለሽ›› ቢሏት ምንም ብትመንን መልአክ ተገልጾ ከነገራት ‹‹ይህ እንዴት ይሆናል?›› ልትል አትችልም፤ እንዴት እንደሚሆንማ ጠንቅቃ ታውቃለችና፡፡ እመቤታችን ከነዚህ ሁሉ ልዩ ስለሆነች ‹‹እፎኑ ይከውነኒ ዝንቱ›› ስትል ፈጽሞ በታተመና እርሱን በሚያልፍ ኅሊና መልአኩን አስጨነቀችው፡፡

 

እርሱም‹‹ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለም›› የምትል ጥቅስ አግኝቶ ፈተናዉን ተገላገለ፡፡ ሌላዉ ቀርቶ በዚህ ጥቅስ ተረትታ ብሥራቱን ስትቀበልም ‹‹ይኩነኒ በከመ ትቤለኒ- እንዳልከው ይሁንልኝ›› ያለች አንት እንዳልከው የአምላኬ ፈቃዱ ሆኖ እንበለ ዘርዕ፣ እንበለ ሩካቤ ከሆነና ተጸንሶ የሚወለደውም እርሱ ከሆነ ይሁን ይደረግ አለች እንጂ ለሌላው ነገርማ ኅሊናዋ እንደታተመ ነው የቀረው፡፡‹‹ ልጄ ሆይ ስሚ፣ እዪ ጆሮሽንም አዘንብዪ፤ ወገንሽን የአባትሽንም ቤት እርሽ፣ ንጉሥ ውበትሽን ወድዶአልና፤ እርሱ ጌታሽ ነውና›› (መዝ 44÷12) ሲል አባቷ ዳዊት በትንቢት እንደተናገረው እርሷ ከሔዋናዊ ጠባይ ተለይታለችና፡፡ ሰሎሞንም‹‹ወዳጄ ሆይ ሁለንተናሽ ውብ ነው ፤ ነውርም የለብሽም፤ ልቤን በፍቅር አሳበድሽው….›› ያለው ለዚህ  ነበር፡፡

 

ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ ‹‹የታተመች ደብዳቤ›› ያላትም ለዚህ ነው/ኢሳ 28 ፤ 12/፡፡ ምክንያቱም ለልማዱ ደብዳቤ ከተጻፈ በኋላ ይታሸጋል፡፡ ስለ እርሷ የተነገረው ግን  ከታተመ ወይም ከታሸገ በኋላ ተጻፈበት የሚል ነው፡፡ አብ በድንግልና አትሞ ሲያበቃ በውስጧ አካላዊ ቃልን የጻፈባት ማንበብ የሚችሉም(እሥራኤል) ማንበብ የማይችሉም(አሕዛብ) እናነበው ዘንድ አንችልም ታትሟልና (በድንግልና በንጽሕና በክብር በምስጢር) አሉ ብሎ የተናገረላት ደብዳቤ እርሷ ናትና፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ጸጋ ለተሰጣቸው ሰዎች ብሥራት ሊያደርስ ሲመጣ ይህ የመጀመሪያው አልነበረም፤ ይሁን እንጂ ለዳንኤልም ሆነ ለጻድቁ ካህን ለዘካርያስ ለእርሷ እንዳደረገው ለእነርሱ መች አደረገ? እነርሱ እጅ ነሱት ሰገዱለት እንጂ እርሱ መቼ እጅ ነሳ ሰገደላቸው? ከዚህ በላይ ልዩ መሆን በእውነት ወዴት ይገኛል፡፡

 

ፍጹም ልዩ መሆኗን ለማስረገጥ ያህል አንድ ነገር ብቻ ላክል፡፡ የጥንቶቹ የቤተክርስቲያን ሊቃዉንት ጌታ ለሐዋርያት ቤተ ክርስቲያንን ይጠብቋት ዘንድ  የሰጠው ሁለት ጊዜ ነው ይላሉ፡፡ አንደኛው ብዙ ጊዜ ሲጠቀስ የምንሰማው ለቅዱስ ጴጥሮስ የተሰጠው ነው፡፡ይህም ‹‹በጎቼን አሰማራ፣ ጠቦቶቼን ጠብቅ እና ግልገሎቼን አሰማራ››/ዮሐ 21፣15-17/የሚለው ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ከዚህ ቀደም ብሎ በመስቀል ላይ የሰጠው ነው፤ በመስቀል ላይ ጌታ ለዮሐንስ ‹‹እነኋት እናትህ›› ሲል የሰጠው እርሷን ብቻ ሳይሆን ቤተ ክርስቲያንንም ነው ይላሉ፡፡

 

በእነዚህ ሊቃዉንት ትርጓሜ መሠርት  ሁለቱም ራሳቸውን የቻሉ ምስጢራትን ይዘዋል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ሕጋዊ ስለነበር(በጋብቻ የተወሰነ ማለት ነው) የተሰጠውም አደራ ይህንኑ የሚመለከትና በጎቹን እስከ ገላግልቶቻቸው(ምእመናን) የሚመለከት ነው፡፡ጌታ በወንጌል ‹‹በጎቼ ድምጼን ይለያሉ›› እንዳለው እነዚህ ድምጽ እንጂ ቃል መለየት የማይቻላቸው ምእመናን ናቸው፡፡  የቅዱስ ዮሐንስ ግን ከዚህ ሁሉ በእጅጉ ይለያል፡፡ምክንያቱም እመቤታችን ራሷ የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ብቻ ሳትሆን የፍጹማን ደናግልም ምሳሌ ናት፡፡ ስለዚህ ከድምጽ ያለፈ ቃላትን ምስጢራትን መለየት የሚቻላቸው ፍጹማንን የሚመለከተው አደራ የተሰጠዉ ለበቃው ብቻ ሳይሆን ለፍጹሙ ድንግል ለዮሐንስ ነዉ፡፡ ስለዚህ እመቤታችንን መግፋት ቤተክርስቲያንን መግፋት ነው፡፡እርሷንም በቤቱ ማስተናግድ የሚቻለው ዮሐንስን የመሰለ ንጹሕ ድንግል ነው፡፡

 

ቅዱስ  ቅዱስ አትናቴዎስ እንደሚለው ጌታ የሰጠው ድንግሊቱን ለድንግል፣ ድንግሉንም ለድንግል፤ ንጹሕንም ለንጹሕ ነው፡፡ መላእክት ሲጠብቋት ከኖሩ በኋላ መልአክ ለመሰለ ሰው ሰጣት እንጂ ለሌላ አልተሰጠችም፤ ሊቀበላት የሚቻለውም የለም፡፡በተለይ ኦሪገን ይህንኑ በተረጎመበት አንቀጹ ስለ ቅዱሱ ብቃት ሲናገር  ለእርሷም ‹‹እነሆ ልጅሽ›› አላት እንጂ ‹‹ልጅ ይሁንሽ›› አላላትም፤ ምክንያቱም ዮሐንስ በዚያ የመከራና የጭንቀት የፍርሃት ቀን በዕለተ ስቅለት ሳይፈራ ሳይሰቀቅ በእግረ መስቀሉ የተገኘው ቅዱስ ጳዉሎስ ‹‹እኔም አሁን ሕያዉ ሆኜ አልኖርም፤ ክርስቶስ ግን በእኔ ይኖራል›› /ገላ 2፣20/ እንዳለዉ ዮሐንስ ራሱን ክዶ ስለነበር ለራሱ እየኖረ አይደለምና በእርሱ የሚኖረው ጌታ ነው፡፡ ‹‹አነሆ ልጅሽ›› ያላትም በእርሱ አድሬ ያለሁት እኔ ነኝ ማለቱ ስለሆነ ከእርሷ ሰው ከሆነ በኋላ ለማንም አልሰጣትም፤ በዮሐንስ አድሮ የተቀበላትም ራሱ ነው፤ ከዚያ በኋላ እርሷን ሊቀበል የሚቻለው የለምና ይላል፡፡ ስለዚህ አንድ ሰው እንኳንስ የእርሷን ነገር ለመንቀፍ ቀርቶ ለማመስገንም ትሰጠው ዘንድ ከፈለገ እንደ ዮሐንስ ራሱን በንጽሕና ይጠብቅ ፣ራሱንም ፈጽሞ ይካድ ባይ ነው፡፡

 

የአሁኖቹ ሰዎች እርሷን ባይቀበሉ፣ በእርሷ አማላጅነት ባያምኑ ለምን እንደነቃለን? እነዚህ በትንሽ ነገር እንኳን መታመን የማይቻላቸው የእርሷን ነገር ይረዱ ዘንድ ታላቁንና ሰማያዊውን ምስጢር ማን አደራ ሊሰጣቸው ይችላል? አንዳንድ የዋኃን ደግሞ መሠርይ ተሐድሶዎች ስለ እርሷ የዘመሯቸውን መዝሙር ተብየ ዘፈኖች እየተመለከቱ ይታለላሉ፡፡ ይህ መናፍቃኑ ስለ እርሷ የሚሉትን መንገድ የተከተለ በእነርሱ ወዝ የታሸ ስለሆነ ተወዳጅ መሥዋዕት አይደለም፡፡ በኦሪት አንበሳው፣ ተኩላው፣ ቀበሮው፣ … የመሳሰለው  አውሬ የገደለውን ሁሉ እንኳን ለመሥዋዕት ልናቀርበው ቀርቶ ልንበላውም የተከለከለ ነው፡፡ ይህም ማለት በመጽሐፍ ቅዱስ የተጠቀሱት አውሬዎች የተባሉት (አጋንንት፣ ርኩሳን መናፍስት፣ መናፍቃን፣…. ደሙን ያፈሰሱትን ወይም በእነርሱ) የተሰዋውን ሁሉ እንኳን ለእግዚኣብሔር ማቅረብ ለእኛም መንካት መርከስ ነው ማለት ነው፡፡ ‹አውሬ የቧጨረውንም አትንካ› የሚል ንባብም ይገኛል፤ ይህ ሁሉ ከእነርሱ የተነካካውን በዚህ ዓለም የዘፈንና የረከሰ መንፈስ የጎሰቆለውን ምንም ለዐይንህ ቢያምርህ (በዘፈን ላደገ ሁሉ የእነርሱ የሚያምረው መሆኑ አይጠረጠርም) ፈጽመህ አትንካ ተብለን ታዘናልና መልከስከስ አስፈላጊ አይደለም፡፡ ግጥሙ በኑፋቄ ዜማው በዘፈን ርኩሰት የተቧጨረ ርኩስ ነውና፡፡እርሷ ቤተ ክርስቲያን ናት፤ የቤተክርስቲያናችንም ስጦታ ስለሆነች በእውነት ልዩ ናትና ይህን በመሰለ መልኩ የተቧጨረውን አናቀርብም፡፡

 

እንግዲህ ዛሬ ተወለደች የምንለው ይህችን ልዩ ድንግል ነው፡፡ስለዚህም የእርሷን በዓለ ልደት ማክበር ከዚህ ሁሉ በረከት መሳተፍ ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔር በእርሷ በኩል ለባሕርያችን ያደረገውንም ክብር ማወቅና መቀበል ጭምር ነው፡፡

 

ከበዓሉ ምን እናገኛለን? የእርሷስ በዓል አልበዛምን?

አንዳንድ ሰዎች በእኛ ቤተክርስቲያን የጌታ በዓል አንሶ የእመቤታችን የበለጠ፤ እኛም ከርሱ ይልቅ ለርሷ የምናደላ የሚመስላቸው ቁጥራቸው በርከት ማለት ጀምሯል፡፡ ያለማወቅ ነውና አይፈረድባቸውም፡፡ ለነቀፋም የተሰለፉ ስለሆነ በ‹ምሰለ ፍቁር ወልዳ-ከተወደደው ልጇ ጋራ› በምንለው ሥዕል ውስጥ እንኳን በሥዕሉ መጠን እየመሰላቸው ጌታ ያነሰ የሚመስላቸው ማስተዋል የራቃቸው ስለሆኑ በእነርሱ አንገረምም፡፡በቤተ ክርስቲያናችን ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፮ ድረስ ከእናቱ ጋር መሰደዱን፣ ከኅዳር ፲፬ ጀምሮ እስከ ልደቱ ይወርዳል ይወለዳል ሲሉ ትንቢት የተናገሩ የነቢያትን ጾም እየጾምን እርሱን እናስባለን፡፡ ከልደት እስከ ዐቢይ ጾም ድረስም በሥጋዌ፤ በአንድነት በሦስትነት መገለጡ አስተርእዮ እየተባለ ይታሰባል ይሰበካል፡፡ ከዚያም ዐቢይ ጾም ይገባል፤ ሁለንተናችን እርሱን በማሰብ ይሰበሰባል፤ ቃለ እግዚአበሔሩም ይህንኑ ያዘክራል፡፡ በትንሣኤውም ሃምሳ ቀናትን እንደ አንድ ቀን እንደ ዕለተ ትንሣኤው በመቁጠር ትንሣኤውን እንሰብካለን፡፡ ከዚህ በማስከተልም ርዕደተ መንፈስ ቅዱስን በዓለ ጰራቅሊጦስን በጾም እናከብራለን፡፡በየወሩም በዓለ እግዚእ፣ መድኃኔዓለም፣ ኢየሱስ፣ አማኑኤል…. እያልን ከዘጠኙ ዓበይትና ከዘጠኙ ንዑሳን በዓላት በተጨማሪ በየአጥቢያቸው የሚታሰቡት ትዝ አይሏቸውም፡፡ ሌላው ቀርቶ በየሳምንቱ ሁለት ቀናትን (ረቡዕ እና አርብ) በጾም ሁለት ቀናትን (ቀዳሚትንና እሑድን) በበዓል ለክርስቶስ መታሰቢያ የሰጠች ብቸኛ ቤተ ክርስቲያን የእኛይቱ ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ብቻ መሆኗን አያስተውሉም፡፡ ይህ ሁሉ ሆኖ ሳለ የማርያም በዓል ከጌታ በዓል ይበልጣል ማለትን ምን ዓይነት አለማስተዋል ልንለው እንችላለን? ቢሆንስ በቅዱሳን በዓል ዋናው ተከባሪ ተመሰጋኝ ማን ሆነና ነው ይሄ ሁሉ ጩኸት? ስለዚህ በዚህም ስም አደረግነው በዚያ እግዚአብሔር በአከበራቸው ቅዱሳን ስም እስካደረግነው ድረስ በዓሉ ሁሉ የእግዚአብሔር ነው፡፡

 

የእመቤታችን በዓለ ልደትም በዚሁ መንፈስ የሚከበር በዓል ነው፡፡ነቢዩ ኢሳይያስ ቀደም ብሎ ‹‹ትወጽእ በትር እምሥርወ እሴይ-ከእሴይ ሥር ወይም ግንድ በትር ትወጣለች››/ኢሳ 11፤6/ ብሎ ስለ ልደቷም ተናግሮላታል፡፡ ይህንንም ሊቁ ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴ ማርያም ዘቀዳሚት ድርሰቱ፤ ‹‹ በትረ ሃይማኖት ዘኢትጸንን ምስማኮሙ ለቅዱሳን-የቅዱሳን መደገፊያቸው ግያዝ የሱነማዊቷን ልጅ ከሞት ያስነሣባት ዘንድ ከነቢዩ ከኤልሳ ተቀብሎ እየተጠራጠረ እንደወሰዳት ያይደለሽ ጽነት ጥርጣሬ የሌለብሽ የሃይማኖት በትር አንቺ ነሽ›› ብሎ ተርጎሞልናል፡፡ አባ ጀሮምም ይህን የነቢዩን ትንቢት በትር ከግንዱ ላይ ተስተካክሎ የሚወጣ ግዳጂ ለመፈጸም የሚፈልግ ስለሆነ የእመቤታችን ልዩ መሆን ያሳያል ይላል፡፡

 

በርግጥም ሊቃውንቱ እንዳሉት ለቅዱሳን መደገፊያ ለአጋንንት ለመናፍቃን ደግሞ ማባረሪያ የሆነች በትር፤ ድንግል ማርያም፡፡ስለዚህ የእርሷን በዓል ማክበር ከዚህ ጥርጣሬ ከሌለው በረከት መሳተፍ ነው፡፡ ይሁን እንጂ በአጠቃላይ የበዓላት ይልቁንም በክርስትና ጥቅማቸው ምንድን ነው የሚለውን እንመልከትና እንፈጽም፡፡

 

በዓላትን በብዛት እንድናከብር ያዘዘን እግዚአብሔር ነው፡፡የምናከብራቸውም ዝም ብለን አይደለም፡፡በተለይም በብሉይ ኪዳን በዓላት ብዙ የመሥዋዕት እንስሳትን ማቅረብና መሠዋት በጥብቅ የሚፈጸም ትእዛዝ ነበረ፡፡ የዚያ ሁሉ መሥዋዕትም ዓላማ ሥርየተ ኃጢኣትን ማስገኘት ነበር፡፡/ዘሌ ፲፯፣፲፩/ በአጭሩ በዓላቱን የማክበሩ ዓላማ ሥርየተ ኃጢኣትን ማሰገኘት ነው ማለት ነው፡፡በዚህ መሠረታዊ ምክንያት በእያንዳንዱ የኦሪት በዓል እጅግ ብዙ የመሥዋዕት እንስሳት ይቀርቡ ነበር፡፡በኦሪት በየዕለቱ ሁለት ሁለት ጠቦቶች፣ በየሰንበቱ ሁለት ተጨማሪ የበግ ጠቦቶች፣በየመባቻው ደግሞ ለየዕለቱ ከሚቀርበው በተጨማሪ ሁለት ወይፈኖች፣ አንድ አውራ በግ፣ ሰባት የአንድ ዓመት የበግ ጠቦቶች፣ አንድ ፍየል ይቀርብ ነበር፡፡ የዓመታዊ በዓላት ደግሞ ከዚህ ሁሉ ይለያል፡፡ለምሳሌ የዳስ በዓሉን ብቻ ብንመለከት ከዕለቱ፣ ከሰንበቱና ከመባቻው እንዲሁም በፈቃድ ከሚቀርቡት በተጨማሪ 73 ወይፈኖች፣ 136 አውራ በጎችና ጠቦቶች፣ 10 አውራ ፍየሎች ይቀርቡ ነበር፡፡ ይህ ሁሉ ግን የእህሉን ቁርባንና ሌላውን መሥዋዕት(ለኃጢኣት ፣ ለበደል፣….የሚባሉትን) ሳይጨምር ነዉ/ዘጸ ፳፱፣፴፰፣ ዘሌ ፳፬፣፭-፱፣ ዘኁ ፳፰፣፱-፲፭፣ዘኁ ፳፱/፡፡

 

‹‹ሕጉ ሊመጣ ያለው የበጎ ነገር እውነተኛ አምሳል ሳይሆን የነገር ጥላ አለውና››/ዕብ 10፣1 / ተብሎ እንደተጻፈ እነዚህ ሁሉ ግን ምሳሌዎች ነበሩ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ከጊዜው የተነሳ አስተማሪዎች ልትሆኑ ሲገባችሁ፥ አንድ ሰው ስለ እግዚአብሔር ቃላት መጀመሪያ ያለውን የሕፃንነትን ትምህርት እንዲያስተምራችሁ እንደ ገና ያስፈልጋችኋልና፤ የሚያስፈልጋችሁም ወተት ነው እንጂ ጠንካራ ምግብ አይደለም።ወተት የሚጋት ሁሉ ሕፃን ስለ ሆነ የጽድቅን ቃል አያውቅምና፤ጠንካራ ምግብ ግን መልካሙንና ክፉውን ለመለየት በስራቸው የለመደ ልቡና ላላቸው ለፍጹማን ሰዎች ነው።›› /ዕብ 5፣ 12-15/ እንዳለው ሊቃውንቱ ለእኛ ወተት ወተቱን እየመገቡ ጠንካራውን ምግብ አላቀረቡልንም ነበር፡፡ አሁን ግን እስኪ ይህን እንኳ እንሞክረው፡፡

 

በኦሪት እንደተጻፈው በፋሲካ የሚሠዋው ልዩ የድኅነት መሥዋዕት በግ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡‹‹በነገው ደግሞ ዮሐንስ ከደቀ መዛሙርቱም ሁለት ቆመው ነበር፥ኢየሱስም ሲሄድ ተመልክቶ። እነሆ የእግዚአብሔር በግ አለ›› /ዮሐ 1፣ 26/።ተብሎ ተጽፎአልና፡፡በሌሎቹ በዓላት የምናቀርባቸው ደግሞ ቀደም ብለን እንዳየነው ወይፈኑ፣ አውራ በጉ፣ ፍየሎቹ(ወንድም ሴትም ነው የሚቀርበው)፣ ሌላው ሁሉ የማን ምሳሌ ነው ማለታችን አይቀርም፡፡ ይህ ሁሉ የበዓል መሥዋዕት የቅዱሳን ምሳሌ ነው፡፡ ‹‹እንደ በጎች ሊበሉን ሰጠኸን፥ ወደ አሕዛብም በተንኸን›› /መዝ 44፣12/ ተብሎ ትንቢትም ተነግሮላቸዋልና።ጌታም በወንጌል ‹‹ስለዚህ፥ እነሆ፥ ነቢያትንና ጥበበኞችን ጻፎችንም ወደ እናንተ እልካለሁ፤ ከእነርሱም ትገድላላችሁ ትሰቅሉማላችሁ፥ ከእነርሱም በምኵራባችሁ ትገርፋላችሁ ከከተማም ወደ ከተማ ታሳድዳላችሁ፤ከጻድቁ ከአቤል ደም ጀምሮ በቤተ መቅደስና በመሠዊያው መካከል እስከ ገደላችሁት እስከ በራክዩ ልጅ እስከ ዘካርያስ ደም ድረስ በምድር ላይ የፈሰሰው የጻድቅ ደም ሁሉ ይደርስባችሁ ዘንድ።እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ሁሉ በዚህ ትውልድ ላይ ይደርሳል›› /ማቴ 23፣35/ ሲል እንደተናገረው ቅዱሳን ለእምነታቸው መሥዋዕት ሆነው ቀርበዋል።ደማቸውንም አንዱ እንደ ፍየል፣ ሌላው እንደ ወይፈን፣ ሌላውም እንደ አውራ በግ አፍስሰዋል፡፡ እነዚህ ሁሉ የመሥዋዕት ዓይነቶች ለተለያየ የኃጢኣት ማስተሥረያ እነደነበሩት እነዚህም ድኅነትን ለመፈጸም ከተሰዋው በግ ከጌታ በኋላ ለምናምን ሁሉ ሥርየተ ኃጢኣትን እናገኝ ዘንድ የሚማልዱ ስለኛም ጭምር ደማቸውን ያፈሰሱ ናቸው፡፡ ይሁን እንጂ የሌላው ጊዜ የመሥዋዕት እንስሳ የፋሲካቀውን በግ ሊተካው እንደማይችልና የመሥዋዕቱም ዓይነት ፈጽሞ የተለያየ እንደ ሆነው ሁሉ የቅዱሳኑ መሥዋዕትነትና ሰማዕትነትም እንዲሁ የተለያየ መሆኑና የእነርሱም የጌታችንንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሊተካ የማይችል መሆኑ ሊዘነጋ አይገባውም፡፡እርሱ ኃጢኣትህ ተሠረየልህ(ሽ) እያለ ይቅር ሲል እነርሱ ግን የሚያስተሠርዩልን እየጸለዩ ነውና፡፡ ከዚህ በመለስ ግን የጥንቶቹ ሊቃውንት እንደተረጎሙልን የእነርሱ ተጋድሎና ሰማዕትነት የእኛ የሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች መሥዋዕቶች ናቸው፤ ስለእነርሱም ሥርየተ ኃጢኣትን እንቀበላለን፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹በመሥዋዕት እንደሚደረግ፥ የእኔ ሕይወት ይሠዋልና፥ የምሄድበትም ጊዜ ደርሶአል  ››/ዕብ 4፣6/ ሲል የተናገረዉው ይህን የሚያረጋግጥልን ነው፡፡

 

ቀደም ብለን እንዳየነው የመሥዋዕቱ እንስሳት የበዙት ለእሥራኤል ለኃጢኣታቸው አስፈላጊ በመሆኑ እንደሆነው ሁሉ በሐዲስ ኪዳን ለምንኖር ለእኛም ብዙ ቅዱሳን መኖራቸው ይጠቅመናል፣ ኃጢኣታቸንም ያስተሠረይልናል፡፡ የመሥዋእቱ እንስሳት በሙሉ የተቆጠሩና የታወቁ እንደሆነው ሁሉ ቅዱሳኑም ምን ቢበዙም እንዲሁ የታወቁና የተቆጠሩ ናቸው፡፡

 

ዳዊት አባታችን ‹‹ዘይኌልቆሙ ለክዋክብት በምልኦሙ፣ ወይጼዉዖሙ ለኩሎሙ በበአስማቲሆሙ- ክዋክብትን በምልዓት ይቆጥራቸዋል፣ ሁሉንም በየስማቸዉም ይጠራቸዋል››/መዝ 146፣4/ ሲል እንደተናገረዉ ክዋክብት የተባሉ ቅዱሳን ሁሉ በእርሱ ዘንድ በባለሟልነት በቃል ኪዳን የታወቁ በመሥዋዕትነትም የተቆጠሩ ናቸዉ፡፡ ያ ሁሉ የ መሥዋዕት እንስሳ ፣ የጧቱና የሰርኩ፣ የሰንበቱና የመባቻዉ፣ የዓመት በዓላቱ፣ የየግለሰቡ የኃጢኣቱ፣ የበደሉ፣ የመንጻቱ፣…በዓይነት በዓይነት እንደሚታወቅ በእርሱም ዘንድ ተቀባይነት እንዳለዉ ሁሉ የየዕለቱ ቅዱሳንም እንዲሁ ይተወቃሉ፤ ጸሎታቸዉና ምልጃቸዉም በእርሱ ዘንድ የከበረ ነዉ፡፡ እመቤታችን ደግሞ ከነዚህ ሁሉ በግንባር ቀደምነት የምትጠራ ልዩ መሥዋዕታችን ናት፡፡በሁለተኛዉ ክፍለዘመን መጨረሻ የነበረዉ የሰረዴሱ መልይጦን/Melito of Sardis/  በፋሲካ መዝሙሩ ላይ እመቤታችንን የመሥዋዕቱን በግ የወለደችልን ንጽሕት ሴት በግ (fair ewe) ይላታል፡፡ ስለዚህ የእመቤታችን በዓለ ልደት ከብሉይ ኪዳን ሰዎች የተሻለ ሥርየተ ኃጢኣት የምናገኝበት ነዉና ከነዚያ በተሻለ በዓላችንን መንፈሳዊ አድርገን እናክብር፤ ከመንፈሳዊ በረከትም እንካፈል፡፡የደራሲዉንም ምስጋናና ምልጃ በመሰለ ምስጋና እንዲህ እንበላት፤‹‹ምንተኑ አዐስየኪ ዕሴተ፤በእንተ ኩሉ ዘገበርኪ ሊተ፤ማርያም ሠናይት ዘታፈቅሪ ምሕረተ፤ሶበሰ ተታአቀቢ ዘዚኣየ ኃጢኣተ፤ እምኢሐየዉኩ አሐተ ሰዓተ›› እያልን ለእርሷ በሚገባ ምስጋና እናመስግናት፡፡ ከዚህ የወጣ ሰዉ በመጀመሪያ እንደተመለከትነዉ ብርሂት ቀኝ ዐይኑን እንደገና እያሳወረ መሆኑን ሊገነዘብ ይገባዋል፡፡ እኛስ ለባሕርያችንን መመኪያ እርሷን የሰጠንን እግዚአብሔርን ‹‹ብርሂት የቀኝ ዐይን ድንግል ማርያምን ›› በዚህ ዕለት የሰጠኸን፣ ከዚህ ዓለም የድንቁርናና የኃጢኣት ጨለማም የገላገልከን ክብር ምስጋና ለአንተ ይሁን፤ አንተ ለመረጥካትና ላከበርካት ለእናትህም ምስጋና ይድረሳት እያልን አፋችንን ሞልተን እናመሰግናለን፡፡ ቀይ ዕንቁ እምነት ገንዘባቸዉ ያልተሰረቀባቸዉ ወይም በአዉሬዉ ዲያብሎስ ያልተቧጨሩት ሁሉ አብረዉን ያመሰግናሉ፡፡ ቀኝ ዐይናችን ሆይ ዛሬም በአንቺ ብርሃን እናያለንና እናመሰግንሻለን፡፡ እንኳን አንቺን አባትሺን አብርሃምን የሚባርኩት እንደሚባረኩ ልጂሽ አስቀድሞ በሙሴ በኩል በኦሪት ነግሮናልና፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡
01

የሕገወጥ ሕግ አስከባሪዎችን ሴራ ያከሸፈ ደብዳቤ

ሚያዚያ 26/2004 ዓ.ም.

ሚያዚያ 24 ቀን 2004 ዓ.ም. ሕገወጥ ሕግ አስከባሪዎች በሚል ርዕስ ሰሞኑን በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስለተፈጸመ ድርጊት ማኅበረ ቅዱሳን መግለጫ ማውጣቱ ይታወሳል፡፡

 

የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ የሆኑት ቆሞስ መልአከ ጽዮን አባ ኅሩይ ወንድይፍራው ሳያምኑበትና ሕጋዊ መስመሩን ሳይጠብቅ በጆቢራዎቹ አቀነባባሪነት የተዘጋጀውን ደብዳቤ ወጪ እንዳይሆን የሚገልጥ ትእዛዝ ለሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ መዝገብ ቤት ሹም ለሆኑት ለወ/ት ዓለምፀሐይ ጌታቸው የላኩትን ደብዳቤ ከዚህ በታች አቅርበናል፡፡

 

01

ማሩ አይምረር፤ ወተቱ አይጥቆር

ሚያዚያ 24/2004 ዓ.ም.

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር ተዋቅሮ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኘው ማኅበረ ቅዱሳን በእግዚአብሔር ፈቃድ አገልግሎቱን ከጀመረ እነሆ ሃያ ዓመታት ተቆጠሩ፡፡ ምንም እንኳን ማኅበሩን በራሳቸው ፈቃደኝነት የተሰባሰቡ ኦርቶዶክሳውያን ቢመሠርቱትም የማኅበሩ መሠረታዊ ዓላማ ግን ቤተ ክርስቲያን ተልእኮዋን ለማሳካት በምታከናውናቸው ተግባራት የልጅነት ድርሻውን ለመወጣት በመሆኑ ወደ ቤተ ክርስቲያን መዋቅር በመግባት መተዳደሪያ ደንቡ በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ በተቀመጠለት ተግባርና ሓላፊነት መሠረት አገልግሎቱን እያከናወነ ያለ ማኅበር ነው፡፡ አባላቱም በሀገር ውስጥም ሆነ በውጪ ሀገራት በቤተ ክርስቲያኗ አጥቢያዎች በሚገኙ ሰበካ ጉባኤያት እና ሰንበት ት/ቤቶች ተመዝግበው የሚጠበቅባቸውን ክርስቲያናዊ ግዴታ እየተወጡ ይገኛሉ፡፡ እነዚህ አባላት አብዛኛዎቹ ቤተ ክርስቲያናቸውን በገንዘብ፣ በዕውቀትና በጉልበት ለማገልገል በፈቃዳቸው ቃል የገቡ ቤተ ክርስቲያንና ሀገሪቷ ካሏት ልዩ ልዩ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ተመርቀው ቤተ ክርስቲያናቸውን አገራቸውንና ወገናቸውን በልዩ ልዩ ሙያ እያገለገሉ የሚገኙ ናቸው፡፡

ማኅበሩ በዋናነት አገልግሎቱን የሚያከናውነው በመተዳደሪያ ደንቡ እንደተቀመጠው አባላቱ በገቡት ቃል መሠረት በየወሩ ከሚሰበሰበው ወርኃዊ አስተዋጽኦ ሲሆን ስብከተ ወንጌል ባልተስፋፋባቸው አካባቢዎች ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት ቅዱሳት መካናትና አብነት ት/ቤቶችን በዘላቂነት በልማት ራሳቸውን ለማስቻል የሚሠሩ ኘሮጀክቶችን በጎ አድራጊ የቤተ ክርስቲያኗ ልጆች ከሆኑ ምእመናንና ማኅበራት ጋር በጋራ በመተባበር ይተገብራል፡፡ ማኅበራችን ባለንት ሃያ የአገልግሎት ዓመታት በእግዚአብሔርም በሰውም ሊታዩና ሊዳሰሱ የሚችሉ በጎ አስተዋጽኦዎችን ለሀገርም ሆነ ለቤተ ክርስቲያን እንዳበረከተ ቢያምንም መሥራት ከሚገባው በጣም ጥቂቱን ብቻ እንደሠራና ገና ብዙ እንደሚጠበቅበትም ይገነዘባል፡፡

እስካሁን ያከናወናቸውን መንፈሳዊና ማኅበራዊ ተግባራት ሲያከናውን ሁሉ ነገር አልጋ በአልጋ ሆኖለት ያለችግርና ውጣውረድ አይደለም፡፡ በእርግጥ አገልግሎቱ መንፈሳዊ አገልግሎት ነውና ሁሉ ነገር ምቹ እንዲሆንም አይጠብቅም፡፡ በየጊዜው የሚገጥሙት ችግሮችና ፈተናዎች የተለያየ መልክ ያላቸው ቢሆኑም የፈተናዎቹ ምንጮች ግን ሁለት ናቸው፡፡ የመጀመሪያው ማኅበሩ የቆመለትን ዓላማና የሚያከናውናቸውን በጎ ተግባራት በዓላማ ከመቃወም የሚመነጭ ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ በተሳሳተ መረጃ ምክንያት ወይም ቀርቦ ባለማየት ከሚፈጠር የተዛባ አመለካከት የሚመነጭ ነው፡፡ ከዚህ አንጻር ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የማኅበሩን አገልግሎት እየገጠሙት ካሉት ችግሮች አንዱ በዘመናችን መላው ዓለምን እያወከው ያለው የአክራሪነት አደጋ በአገራችንም ያለውን አሉታዊ ተፅዕኖ ለማሳየት በሚደረጉ ገለጻዎችና የውይይት መድረኮች ግልጽ ባልሆነና በማይወክለው መንገድ የማኅበሩን ስም በመጥቀስ በበጎ አስተዋጽኦው ላይ ጥላ የሚያጠላ ስሜት መፈጠሩ ነው፡፡ ይህ የተዛባ ሥዕል በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በተለያየ መጠንና በተለያየ መንገድ ሲገለጽ መቆየቱና አሁንም እየተገለጸ መሆኑ በአባላቱም ሆነ በሌሎች ምእመናን ዘንድ መደነጋገርን መፍጠሩ አልቀረም፡፡ ምክንያቱም አባላቱም ሆኑ ሌሎች ምእመናን ከከተማ እስከ ገጠር የሚያውቁት የማኅበረ ቅዱሳን ማንነትና ምንነት አሁን እየተባለ ካለው ጋር ፍፁም የማይገናኝ በመሆኑ ነው፡፡

በመግቢያው ላይ እንደተገለጸው ማኅበረ ቅዱሳን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ የመጨረሻ መዋቅር በሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ መተዳደሪያ ደንብ ጸድቆለት፣ የቤተ ክርስቲያኗን መዋቅራዊ አሠራር ተከትሎ እየሠራ ያለ፣ በርቀት ላሉ በሚሠራቸው ሥራዎች ራሱን የሚገልጥ፣ ቀርበው ማየትና ማወቅ ለሚፈልጉ የሚዳሰስና የሚጨበጥ አካል ያለው መንፈሳዊ ማኅበር ነው፡፡ በመተዳደሪያ ደንቡ ላይ ባለው ግልጽ አቋሙ እንዳስቀመጠው በማንኛውም የፖለቲካ እንቅስቃሴ ውስጥ ጣልቃ አይገባም፡፡ ከተሰጠው ዓላማና ተግባር እና ከቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ አገልግሎት አንጻር አቋሙን መግለጽ ሲያስፈልገው የሚገልጽባቸው የራሱ ሚዲያዎች ያሉት ማኅበር ነው፡፡ የአክራሪነት አደጋ በሀገርም ሆነ በቤተ ክርስቲያን ላይ ስለሚያደርሰው ጥፋት፣ መልካም የሆነው የሰዎች እርስ በርስ ተከባብሮ የመኖርን የቆየ አገራዊ እሴት ስለማስቀጠል፣ አገራቸውንና ወገናቸውን በታማኝነትና በቅንነት የሚያገለግሉ ዜጎችን ስለማፍራት እንደ ቤተ ክርስቲያኗ አስተምህሮ ሓላፊነት በተሞላው መንገድ ሲያስተምርና ሲሠራ ኖሯል፤ አሁንም እየሠራ ነው፡፡ ወደፊትም ያስተምራል ይሠራልም፡፡ እንኳን እምነትን ያህል ታላቅ ነገር ይቅርና አንድ ሰው የሚከተለውን ፍልስፍና ሊከተለው የሚችለው ትክክል ነው ብሎ ሲያምን ብቻ ነው፡፡ አንድ ሰው ዛሬ በምድር ላይ ሲኖር የሕይወቴ መርሕ አድርጌ የምጓዝበት ከሞት በኋላም ዘላለማዊ ሕይወት የምወርስበት እምነት /ሃይማኖት/ ትክክል ነው ብሎ ማመኑ በምንም መስፈርት አክራሪነት ሊባል አይችልም፤ ምክንያቱም የእኔ ትክክል ነው ማለት የሌላው ትክክል አይደለም ወይም የእኔ ብቻ መኖር አለበት የሌላው መኖር የለበትም ማለት ሊሆን አይችልምና፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትክክል ናት ብሎ ያምናል፤ እንዴት ትክክል እንደሆነች በንግግርም በግብርም ይገልጣል፤ ይህ ትክክል የሆነው ሁለንተናዊ ማንነቷ ተጠብቆ እንዲኖርም የድርሻውን ይወጣል፡፡ ይህ አስተሳሰብ በምንም መንገድ ሌላውን የማጥፋት መንፈስን ያዘለ አክራሪነት ተብሎ ሊተረጎም አይችልም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ለአገሪቱ ሁለንተናዊ ማንነትና ዕድገት የነበራትን በጎ አስተዋጽኦ መግለጽም ሆነ ዛሬም ይህንን አስተዋጽኦዋን እንድትቀጥል ማድረግ እንደ ክርስቲያንም ሆነ እንደ ዜጋ የሚጠበቅበት ተግባር መሆኑን ማኅበራችን ያምናል፡፡ በመሆኑም ዓለምን የሁከትና የሰቆቃ መናኸሪያ እያደረጋት ያለው አክራሪነት ማኅበራችንን አይገልጠውም፡፡ ይልቁንም ሙስና፣ አለመታመን፣ ወንጀለኝነት፣ በሽታ ፣ ወዘተ  እያተራመሳት ባለችው ዓለም ከተለያዩ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተመርቀው በልዩ ልዩ ሙያ አገራቸውንና ወገናቸውን በቅንነት፣ በታማኝነትና በእውነት የሚያገለግሉ ዜጎችን በማፍራት በራሱ ፈቃድ፣ በራሱ ገንዘብና ጉልበት የበኩሉን እያበረከተ የሚገኝ ማኅበር አገራዊ አስተዋጽኦው በሁሉም ዘንድ በበጎነቱ ጎልቶ ሊበረታታ ሊደገፍ ይገባዋል እንጂ ገጽታውን የሚያጠቁር ማንነቱን የሚያዛባ ሥዕል በመሳልና መደነጋገርን መፍጠር ተገቢ አይመስለንም፡፡

በመጨረሻም ማኅበረ ቅዱሳን ጉድለት ካለበትም ስለ ጉድለቱ በምድራዊም ሆነ በሰማያዊ ሕግጋት ሊጠየቅ የሚችል ሕጋዊ መንፈሳዊ ተቋም እንጂ ምንም የተሠወረ ነገር እንደሌለ አምነን አባላቱም ሆነ ምእመናን ዛሬም እንደ ትላንቱ አገልግሎታችንን አጠናክረን እንድንቀጥል አደራ በማለት በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ማኅበሩን በማይገልጸው ማንነት እየሣልን ያለን አካላት ደግሞ ማሩን ባለማምረር ወተቱን ባለማጥቆር የማኅበሩን አገራዊ አስተዋጽኦ እናበረታታ ዘንድ ማኅበራችን መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡

ሕገ ወጥ ሕግ አስከባሪዎች

ሚያዝያ 24/2004 ዓ.ም.

ከሰሞኑ ለሰሚ የሚያሳፍር፤ አንድ ጉዳይ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ተፈጽሟል፡፡ ጉዳዩን በአንክሮ ለተመለከተው በእጅጉ ያሳስባል፡፡ የሰላ አንደበት ይዘው ያልኾኑትን ነን በማለት የሌላቸውን ሥልጣንና ዕውቀት እንዳላቸው በማስመሰል ደግ አባቶችን የሚያታልሉ፤ ከቤተ ክርስቲያን ጥቅም ይልቅ የራሳቸውን የሚያስቀድሙ ወረበሎች አሉ፡፡ እነዚህ ጆቢራዎች በደጋግ አባቶቻችን አእጋር ሥር እየተርመሰመሱ፤ ዕውቀት መንፈሳዊ ሳያቋርጥ የሚያፈሰውን የእናት ቤተ ክርስቲያን ጡት እየጠቡ አድገውና ጐልምሰው ሊያገለግሉ በተሰበሰቡ ሊቃውንት መካከል እየተሹለከለኩ ተንኮላቸውን ያለድካም ለመፈጸም ሲኳትኑ ይታያሉ፡፡ ከሰሞኑ የሰማነው ግብዝነትን ከአላዋቂነት ጋር አስተባብሮ የያዘ ከንቱ ተግባር፤ እነዚሀን መሰሪዎች አበው በበሰለ አመራራቸው ለይተው በመጠረቅ ከጉያቸው የሚያባርሩበት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንም በዕውቀት ሚዛን መዝነው ማኔ ቴቄል ፋሬስ ብለው ለይተው የሚጥሉበት ሰዓት ከመቼውም ጊዜ በበለጠ መድረሱን የሚያመለክት ነው፡፡ ጊዜ ለሚሰጠው እንጂ ለማይሰጠው ጉዳይ መዘግየት ጉዳቱ ለራስ ነውና፡፡

ጉዳዩ በማኅበረ ቅዱሳን እንቅስቃሴ ጥቅማቸው የተነካ ወይም የሚነካ በመሰላቸው ሰዎች ተቀነባብሮ የነበረ ሴራ ነው፡፡ እነዚህ ግለሰቦች ማኅበሩ በአባቶች መመሪያና ምክር እንዲሁም ጸሎት እየታገዘ የነበረ አገልግሎቱን በተጠናከረ መንገድ ቀጥሎ ባለበት በአሁኑ ጊዜ ከሕግና ትእዛዝ ፍጹም እንደወጣ አድርገው በማቅረብ በአገልግሎቱ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ የሚያመጣ ደብዳቤ ተፈርሞ እንዲበተን ለማድረግ ያደረጉት ከንቱ ሙከራ ነው፡፡ ግለሰቦቹ ይህንን እኩይ፣ በእግዚአብሔርና በሰው ሕግጋት የሚያስጠይቅ ተግባር ለማሳካት ያላደረጉት ጥረት ለአባቶችም ያልቀባጠሩት ማሳመኛ የሚመስል ነገር የለም፡፡ የእኩይ ተግባራቸው መነሻ ያደረጉት ለማኅበሩ እንዲደርስ ያሉትን ማሩን የሚያመር ወተቱን የሚያጠቁር የክስ ደብዳቤ ማርቀቅ ነው፡፡ ለደብዳቤው ርዕሰ ጉዳይነት የመረጡት ዐረፍተ ነገር «ለሕግ የበላይነት ሥልጣን ታዛዥ ሆኖ አለመገኘትን በሚመለከት ይሆናል» የሚል የአማርኛ ሰዋስው ሀሁን ያላለፈ በዚህም የጆቢራዎቹን ማንነት የገለጠ ያልተሟላ ዐረፍተ ነገር ነው፡፡ በዚህ ርዕሰ ጉዳይነት የታሠረው ከንቱ ደብዳቤ በወግ ባልተጻፈ፤ ርዝመታቸው በትልልቅ አናቅጽ ማሠሪያ የተገታ ከሳሽ ዐረፍተ ነገሮች ታጅሏል፡፡ የደብዳቤው ፍሬ ሐሳብ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ፊርማ በጸደቀ ደንብ የተቋቋመው፤ በደንቡም ብቻ ሳይኾን በየዕለቱ በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዐን አበው ተግሣጽ፣ ምክርና መመሪያ እየታገዘ አገልግሎቱን እየፈጸመ ያለው ማኅበረ ቅዱሳን ከቤተ ክርስቲያኗ ማእከላዊ አስተዳደር ቁጥጥር ውጪ ነው፤ በዚህም የሚሰጠውን መመሪያ ለመቀበል ፈቃደኛ አልኾነም የሚል ነው፡፡ ደብዳቤው ይኽንኑ እንቢተኝነት ለመቀልበስ በቤተ ክርስቲያኗ አስተዳደርና በማኅበሩ መካከል «በዕለት፣ በሳምንት፣ በወርና በዓመት ያልተገደበ የመጻጻፍ ተግባር» ሲካሔድ እንደቆየ ያትታል፡፡ ደብዳቤ መጻጻፉ አሁንም «ከመቼውም ጊዜ ጐልቶ የታየበት ወቅት» እንደኾነም ያስረግጣል፡፡ ይህም የማኅበሩን «የበላይ ተጠሪ የሆነውን የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያን» ለወቀሳ የዳረገ መኾኑን ይጠቅስና፤ ማኅበሩ በዚህ ተግባሩ የመምሪያውንም ኾነ የቤተ ክርስቲያን ማእከላዊ አስተዳደር ህልውና እየተፈታተነ እንደኾነ በሬ ወለደ አሉባልታውን ይነዛል፡፡ ለዚህም ማሥረጃ ይጠቅሳል፡፡

መስከረም 12 ቀን 2002 ዓ.ም «ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ በጠቅላይ ቤተክህነት የየመምሪያውና ድርጅቶች ሓላፊዎች እንዲሁም የማኅበሩ ሥራ አመራርና ሥራ አስፈጻሚዎች ወዘተ በተገኙበት የተሰጠውን ባለ 6 ነጥብ «የሥራ አፈጻጸም መመሪያ» ተግባራዊ ለማድረግ ፈቃደኛ አይደለም ይላል፡፡ በማከልም በዚህ የተነሣ ለደረሰው ችግር ማኅበሩን ተጠያቂ በማድረግ፤ ጉዳዩ በቤተ ክርስቲያኗ «ሊኖር የሚገባውን የሥልጣን ተዋረድ የሚሸራርፍ ሆኖ ከመታየቱም በላይ የማእከሉን አስተዳደርና ኃላፊነት ድርሻ የሚጐዳ አካሔድ ያለው» ነው ይልና፤ የማኅበሩ አልታዘዝ ባይነትና ሕጋዊ ያልኾነ እንቅስቃሴ በፍጥነት መታረም እንዳለበት ታምኖበታል ይላል፡፡ ደብዳቤው ይህንን ሁሉ ካለ በኋላ መመሪያ ወደ ማውረድ ይገባል፡፡ «ስለዚህ ይህ ደብዳቤ በደረሳችሁ ከ10 ቀናት ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ ቀደም ሲል መስከረም 12 ቀን 2002 ዓ.ም በምልዓተ ጉባኤ ተወስኖ በተላለፈላችሁ ቃለ ጉባኤ የተቀመጡትን ስድስት ነጥቦች ተግባራዊ እንድታደርጉ እያስገነዘብን በተሰጠው የጊዜ ገደብ ተጠናቆ ካልቀረበ ግን በቤተ ክርስቲያኒቱ መመሪያዎች የተቀመጠውን ድንጋጌ ለማስከበር ሲባል አስተዳደራዊ እርምጃ እንዲወሰድ የሚደረግ መሆኑን እናስታውቃለን» በማለት መመሪያውን በማዥጐድጐድ  ያጠቃልላል፡፡

ጆቢራዎቹ ይህንን ደብዳቤ አርቅቀው በኮምፒውተር ከጨረሱ በኋላ ቀጣይ ከይሲያዊ ተግባራቸው ያደረጉት፤ ደብዳቤው በማደራጃ መምሪያው ሓላፊ ፊርማ ለማኅበሩ እንዲሰጠው ነውና ዓላማው፤ የመምሪያው ሓላፊ ላይ ተጽዕኖ የሚያደርግ ድምጽ ወደ መፈለግ ገቡ፡፡ አወጡ አወረዱ፡፡ ተጽዕኖ ሊፈጥሩ ይችላሉ ወዳሏቸው አባትም ምላሳቸውን አስረዝመው፣ አለባበሳቸውን አሳምረው፣ ያሳምናል ያሉትን ውሸት ቀምረው ቀረቡ፡፡ ቀመራቸው ቅዱስ ፓትርያርኩ ደብዳቤ እንዲጻፍ አዝዘዋልና የመምሪያ ሓላፊው በተዘጋጀው ደብዳቤ እንዲፈርሙ ትእዛዝ ይስጡ የሚል ነበር፡፡ ደጉ አባትም የጆቢራዎቹን ቃል ሰምተው የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊን ጠርተው እንዲህ ዓይነት ደብዳቤ ተዘጋጅቷልና ይፈርሙ ይሏቸዋል፡፡ በጉዳዩ ግራ የተጋቡት የመምሪያው ሓላፊም ደብዳቤውን ሲያነቡ በእሳቸው ስም ሊወጣ የማይችል መኾኑንና ለጉዳዩም እውቅና እንደማይሰጡ መመሪያውን ለሰጧቸው አባት ይገልጻሉ፡፡ በዚህ ሂደት ጆቢራዎቹ ያሰብነው ተሳካ በሚል በመረጡት ሆቴል ፌስታ ያደርጋሉ፡፡ ሁለቱ አባቶች ግን ተመካክረው ጉዳዩ እንዲዘገይ ያደርጋሉ፡፡ በዚህ ሒደት ሌሎች የቤተ ክርስቲያኗ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ይሰሙና ጉዳዩን አዝዘው እንደኾነ ቅዱስ ፓትርያርኩን ይጠይቃሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት ማኅበሩን ዕለት ዕለት እያቀረቡ በመምከር ላይ ያሉት ቅዱስነታቸውም በእሳቸው ስም በተሠራው ወንጀል አዝነው ደብዳቤው ተሠራጭቶ እንደኾነ በአስቸኳይ እንዲሰበሰብ ያዝዛሉ፡፡ የጆቢራዎቹ ከይሲያዊ እንቅስቃሴ በዚህ መንገድ ተኮላሸ፡፡ እውነት የለውምና፡፡

ለመኾኑ ጆቢራዎቹ እነማን ናቸው?

ይህ ከባድ ወንጀል በማኅበሩ ላይ ስለተፈጸመ ሳይኾን ድርጊቱ በቤተ ክህነታችን ውስጥ እየተፈጸመ ስላለውና ወደፊትም ሊፈጸም ከሚችለው ከባድ ጥፋት አንጻር ስለነዚህ ግለሰቦች ወደፊት በዝርዝር እናሳውቃለን፡፡

በመሠረቱ ማኅበረ ቅዱሳን በሁሉም የቤተ ክህነት ደረጃ ሕግ እንዲከበር ይፈልጋል፡፡ ለዚህም ለሕግና ሥርዓት መከበር ቀዳሚ ሓላፊነት ካለባቸው አባቶች ጋር በየጊዜው ይመካከራል፡፡ ቢኾን የሚለውንም በልጅነት ያቀርባል፡፡ ማኅበሩ ይህንን የሚያደርገው ራሱ አባቶች በሰጡት መመሪያ መሠረት ለመሄድ የቻለውን ሁሉ በማድረግ ነው፡፡ በዚህም ጆቢራዎቹ መደረግ አለበት ብለው ያወረዱትን «ትእዛዝ» ቀድሞም ሲያደርገው የነበረው፣ አሁንም እያደረገ ያለው ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ምስክሮቹ ማኅበሩን መመሪያ በመስጠትና እንቅስቃሴውን በመከታተል የሚያሠሩት አባቶች ናቸው፡፡

ማኅበሩ ዘወትር እንደሚለው፤ የቤተ ክርስቲያኗን ማእከላዊ አስተዳደር ጠብቆ በአባቶች መመሪያና ቁጥጥር እንደሚሠራ ምንም ዓይነት ብዥታ ሊኖር አይገባም፡፡ ሕግን አክብሮ በቤተ ክርስቲያኗ ሕግ እንዲከበር በተግባር የሚታገል ነውና፡፡ አሁንም ቤተ ክርስቲያኗ በምትጠይቀው አግባብ ሁሉ ራሱን ለማሳየት ዝግጁ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን ለቤተ ክርስቲያን የተቋቋመ ነውና፡፡ ነገር ግን በማይመለከታቸው እየገቡ አባቶችን በማታለል ለሚሠነዘርበት ጥቃት አበውን ምስክር በማድረግ ምላሹን እየሠጠ ይሄዳል፡፡

ከማኅበሩ አልፎ ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የኾነው የሰሞኑ የማታለል ተግባር በቤተ ክህነታችን እየኾነ ያለው አሳሳቢ H#ኔታ መገለጫ ነው፡፡ አባቶቻችን የነገርን ሁሉ በጐ ገጽታ መመልከትን ሀብት ያደረጉ እንደኾነ ይታወቃል፡፡ ወንጌል ለአነዋወራቸው ሁሉ መመሪያ ነውና፡፡ ነገር ግን ይህንን የዋሕነታቸውን ተጠቅመው በረዘመ ምላሳቸውና ራሳቸውን ለራሳቸው በሚፈጥሩት ከፍ ያለ ማንነታቸው በስማቸውና በፊርማቸው ወንጀል እንዳያሠሯቸው እንሰጋለን፡፡ ለዚህ ተግባራቸውም እውነትን ይዘው ከቆሙ ሊቃውንት ጋር ራሳቸውን አመሳስለው በአበው እግር ሥር መርመስመሳቸውን እናያለን፡፡ ይህ በቤተ ክህነታችን ሥር እያንዣበበ ያለው አደጋ በሁለም ጥረት በኖ ሊጠፋ ያስፈልጋል፡፡ ይህንን ዕውን ለማድረግ በሚደረግ ማንኛውም እንቅስቃሴ ማኅበራችን ንቁ ተሳትፎውን ይቀጥላል፡፡ ለዚህም የአባቶቻችን ምክርና መመሪያ እንደማይለየው ያምናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር