በጎ አድራጊ ምእመናን ለማኅበሩ ሕንፃ ግንባታ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ አደረጉ፡፡

ግንቦት 22/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

•    የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር በዮድ አቢሲንያ ተካሄዷል፡፡
•   “ቅዱስ ሲኖዶስ ከእናንተ ጋር ነው፡፡”ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ
•   “ይህን ቤት ለመሥራት የነበረው ውጣ ውረድ፣ የደረሰባቸሁ መከራ ብ
ዙ ነው፡፡ ብዙውን ፈተና አልፋችሁታል፡፡” ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ፡፡

በግንባታ ላይ የሚገኘውን የማኅበረ ቅዱሳን ጽ/ቤት ሕንፃ ማስፈጸሚያ የሚውል በበጎ አድራጊ ምእመናን አነሣሽነትና አስተባባሪነት ሰኞ ግንቦት 20 ቀን 2004 ዓ.ም. ቦሌ በሚገኘው ዮድ አቢሲንያ የባሕል ምግብ ቤት የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር ተካሄደ፡፡መርሐ ግብሩ በብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የደቡብ ትግራይ ማይጨው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በጸሎት የተከፈተ ሲሆን ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ረዳትና የሰሜን ሸዋ ሰላሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እንዲሁም ብፁዕ አቡነ ፊሊጶስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ የኢሉባቦርና የጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ ማኅበረ ቅዱሳንንና የማኅበረ ቅዱሳንን እንቅስቃሴ ለመደገፍ በራሳቸው ፍላጎት የተሰበሰቡትን በጎ አድራጊ ባለሀብቶችንና ምእመናንን አመስግነዋል፡፡ በሰጡት ቃለምእዳን፡፡ “መንፈሰ ጠንካሮች ሁኑ፣ በማንኛውም በኩል እንዳትበገሩ፡፡ እኛ በእናንተ ልበ ሙሉ ነን፡፡ እምነታችሁ ጠንካራ ነው፡፡ ሃይማኖት ካለ ማንኛውንም ነገር መሥራት ይቻላል፡፡ እንመካባችኋለን፡፡ ከእኛ ይልቅ ቤተ ክርስቲያንን ትጠብቃላችሁ፡፡ ይህ ቤት ለመሥራት የነበረው ውጣ ውረድ፣ የደረሰባችሁ መከራ ብዙ ነው፡፡ ብዙውን ፈተና አልፋችኋል፡፡ በዚህ ሳልፍ በጅምር ያለውን ሕንፃ እያየሁ ገንዘብ አጡ ማለት ነው? አቃታቸው እያልኩ ከራሴ ጋር እሟገት ነበር፡፡ ረዳት አጡ? መቼ ይሆን የሚፈጸመው? እነዚህ ልጆች ያሳፍሩን ይሆን እንዴ እያልኩ እሟገታለሁ፡፡ እኔ ተሸጬ ሁሉም ነገር በሆነ፡፡ ሽማግሌን ማን ይገዛል? እግዚአብሔር ሆይ እርዳቸው፣ ቅድስተ ቅዱሳን በደጅሽ ነው ያሉት በረድኤትሽ እርጃቸው እያልኩ ስጸልይ ነው የኖርኩት፡፡ ተስፋ አለን፡፡ ዛሬ የተሰበሰባችሁት ትጨርሱታላችሁ” በማለት አባታዊ ምክራቸውን ለግሰዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ፊልጶስም በሰጡት ቃለ ምእዳን እነዚህ ልጆቻችን በትእግሥት ሁሉን አሳልፈው፣ ድል መትተው፣ ድል ተጎናጽፈው እዚህ በመድረሳቸው እግዚአብሔር ከእነሱ ጋር መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው፡፡ ሰው የሚታወቀው በሥራው በእምነቱ፣ በአቋሙ ነው፡፡ እነዚህ ልጆቻችን ካየናቸው ጊዜ ጀምሮ ወደ ኋላ ያላሉ እንደብረት ምሰሶ የሆኑ፣ አንድነታቸውን አጠናክረው አዋሕደው ወደፊት እንጂ ወደ ኋላ የማይሉ፣ የመጣባቸውንና የሚመጣባቸውን ሁሉ ፈተና በጣጥሰው ያለፉና የሚያልፉ ለሁላችን አብነት የሚሆኑን ለቤተ ክርስቲያናችን መኩሪያና መመኪያዎች ናቸው፡፡ ታግለው ሩጠው እዚህ በመድረሳቸው እግዚአብሔርን ልናመሰግን ይገባል ብለዋል፡፡ ብፁዕነታቸው አያይዘውም ማኅበረ ቅዱሳን ልጆቻችን 20 ዓመታትን ታግላችሁ አልፋችሁ እዚህ ደርሳችኋል፡፡ ወደፊት ደግሞ የት እንደምትደርሱ እግዚአብሔር ያውቃል፡፡ በርቱ ጠንክሩ፡፡ በርትታችሁ ከሠራችሁ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከእናንተ ጋር ነው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ከቅዱስ ፓትርያርኩ ጀምሮ ከእናንተ ጋር ነው፡፡ ከእናንተ ጋር ይሠራል በማለት ማኅበሩን ያበረታቱ ሲሆን በጎ አድራጊ ምእመናን አስመልክቶም እግዚአብሔር በሰጣችሁ ለቤተ ክርስቲያናችሁ፣ ለእምነታችሁ ለታሪካችሁ፣ ለባሕላችሁና ለቅርሳችሁ ካላችሁ ላይ መስጠት፣ መለገስ እናንተን ብፁዓን ያሰኛችኋልና ስጡ ብለዋል፡፡

 

የመርሐ ግብሩ አስተባባሪና የበጎ አድራጊዎቹ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ደርቤ ሥነ ጊዮርጊስ መርሐ ግብሩ የተዘጋጀበት ዋነኛ ምክንያት ሲገልጹ “ ማኅበረ ቅዱሳንን ለአራት ዓመታት ያህል በጥልቀት የሚሠራውን ሥራ ለመከታተል ጥረት አድርገናል፡፡ ምንድነው የሚሠሩት? እንዴት ነው ሥራቸውን የሚሠሩት ብለን አጠናን፡፡ 7 የቤተ ክርስቲያን ወንድማማቾች በመሠባሰብ ውይይት አደረግን፡፡ እንዴት ዝም ብለን እንመለከታለን? ይህ ሕንፃ ከተጀመረ 10 ዓመት ሞላው፡፡ ሊጨርሱት አልቻሉም ስለዚህ ለምን እኛ አናስጨርሳቸውም? በማለት የማኅበሩን ጥረት ለማገዝ ተስማማን፡፡ በጀታቸውን ለገዳማትና አድባራት፣ ለአብነት ትምህርት ቤቶች ለሕንፃ ግንባታ ያውሉታል፡፡ ሥራቸውን እየሠሩ ያሉት አቧራ እየጠረጉ ነው፡፡ የምንችለውን ሁሉ አድርገን ይህንን ሕንፃ እናስጨርሳቸው የሚል ዓላማ ያዝን ወንድማችን አቶ ትእዛዙ ኮሬ የዮድ አቢሲንያ የባሕል ምግብ ቤት ባለቤትም `ምእመናንን አሰባስቡ የምግብ ቤቱን አዳራሸና ሙሉ የምሳ ወጪውን እችላለሁ´ በማለቱ የዛሬውን የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር አዘጋጀነው፡፡” በማለት ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም  20 ዓመታት ምንም ሳይረዱ እዚህ ከደረሱ ሕንጻውን አስጨርሰን የቢሮ መሣሪያዎችን ብናሟላላቸው፣ ከጀርባቸው ሆነን ከደገፍናቸው ታላቅ ሥራ ይሠራሉ ብለን እናምናለን፡፡ ማኀበረ ቅዱሳን በእሳት የተፈተነ ወርቅ ነው፡፡ በዚህ ዘመን የተሰጠን ታላቅ ማኅበር ነው፡፡ በጸሎታችሁ ማኅበሩን ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ የምንችለውን ሁሉ አድርገን ማኅበሩን እንደግፍ፣ ከጎኑ እንሰለፍ፡፡ ይህ ኮሚቴ እስከ መጨረሻው ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር ለመጓዝ ወስኗል ብለዋል፡፡

 

የዮድ አቢሲንያ የባሕል ምግብ ቤት ባለቤት አቶ ትእዛዙ ኮሬ በበኩላቸው የዛሬውን መርሐ ግብር ለማዘጋጀት ምን እንዳነሳሳቸው ሲገልጹ ሁላችንም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ልጆች ነን፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን የሚሠራውን ሥራ በቅርበት ስንከታተል ቆይተናል፡፡ በየገዳማቱ ያሉትን ችግሮች ለማቃለል፣ የአብነት ት/ቤቶችን ለማጠናከር እያደረገ ያለው ጥረት ተመልክተናል፡፡ ከወር ደመወዛቸው እየቆጠቡ የሚያደርጉትን በመመልከት በተለይም በንግዱ ውስጥ ያለነው የቤተ ክርስቲያን ልጆች እንዴት እንርዳቸው በማለት ለሚፈጽሙት በጎ ሥራ ለማገዝ ነው የተነሳነው፡፡ አቅም በፈቀደ መጠን የድርሻችንን ለመወጣት ይህ ጅምር ነው፡፡ ወደፊት ብዙ ነገሮችን በጋራ እንሠራለን በማለት ገልጸዋል፡፡

 

ቀሲስ ዶ/ር ሰሙ ምትኩ ቤተ ክርስቲያናችን ወደፊት ምን ደረጃ ላይ መድረስ እንደሚገባት ያመለከተ ጥናት በአጭሩ አቅርበዋል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሁል ጊዜ ስንዱ እመቤት ናት፡፡ የጎደላት አለ አንልም፡፡ ነገር ግን ሁለንተናዊ እድገት ያስፈለጋታል፡፡ እድገቱ የሁላችንም እንደሆነና እኛም ቤተ ክርስቲያን ሆና እንድናያት የምንመኘው ደረጃ እንድትደርስ መጣር አለብን ቤተ ክርስቲያናችን ሁለንተናዊ እድገት ያስፈልጋታል ያሏቸውን ዝርዝር ነጥቦችን በመጥቀስ አቅርበዋል፡፡

 

ዶ/ር የራስ ወርቅ አድማሴ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የመጡትን ምሁራንን በመወከል ባሰሙት ንግግር እንደ ማኅበረ ቅዱሳን ያለ የተደራጀ አካል ሲኖር ቤተ ክርስቲያናችንን ከአደጋ ለማዳን ከጎኑ ልንሆን ይገባል፡፡ ምሁራን የነፃ እውቀት አገልግሎት በመስጠት፣ ባለሀብቱ ደግሞ ገንዘብ በመለገስ ከፍተኛ ሥራ መሥራት ይቻላል፡፡ የሁኔታዎች መቀያየር ከግንዛቤ በማስገባት በፍጥነት ያለንን የአእምሮ፣ የገንዘብና የጉልበት ኀይል አስተባብረን ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር አብረን መሥራት አለብን በማለት ገልጸዋል፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ላይ የገቢ ማሰባሰቢያ የቃል ኪዳን መግቢያ ሰነድ በአስተባባሪ ኮሚቴው ተሠራጭቷል፡፡ ምእመናንም እንደ አቅማቸው ምላሻቸውን ሰጥተዋል፡፡ በመጋቤ ሐዲስ እሸቱ አለማየሁ የወንጌል ትምህርት የተሰጠ ሲሆን “ለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት አብረን እንሥራ” በሚል ርእስ በቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የተዘጋጀ ገዳማት በአሁኑ ወቅት ያሉበትን አሳሳቢ ሁኔት የሚያስቃኝ ዘጋቢ ፊልም ቀርቧል፡፡ እንዲሁም ተዋሕዶ የተሰኘ መንፈሳዊ ድራማ በታዋቂ አርቲስቶች የቀረበ ሲሆን ሊቀ መዘምራን ኪነጥበብ ወ/ቂርቆስና ዘማሪት ማርታ ኀ/ሥላሴ ያሬዳዊ ዝማሬ አቅርበዋል፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይ ጥሪ የተደረገላቸው ታላላቅ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ምሁራን፣ ባለሀብቶችና ምእመናን የተገኙ ሲሆን በሊቃነ ጳጳሳት ቡራኬና ጸሎት መርሐ ግብሩ እንደ ተጠናቀቀ የምሳ ግብዣው ተካሂዷል፡፡

Yemeba Serchet to Monks

ለገዳማት የመብዐና አልባሳት ድጋፍ ተደረገ

በእንዳለ ደምስስ
ግንቦት 18/2004 ዓ.ም.

በቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል በየወሩ እየተዘጋጀ የሚቀርበው የዜና ገዳማት መርሐ ግብር ግንቦት 7 ቀንYemeba Serchet to Monks 2004 ዓ.ም. ተካሔደ፡፡ በዋነኛነት ከየካቲት 24 እስከ መጋቢት 4 ቀን 2004 ዓ.ም. ድረስ በቆየው የመብዐ ሳምንት በሚል በችግር ላይ ለሚገኙ 400 አድባራትና ገዳማትን ለመርዳት ከምእመናን የተሰበሰበን መብዐ እና አልባሳት /ልብሰ ተክህኖ/ ስርጭት ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ 800 ሺህ ብር ለመሰብሰብ የተቻለ ሲሆን እስከ 750 ምእመናን ተሳትፎ አድርገዋል በማለት የገለጹት የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ መሠረት ናቸው፡፡ በተገኘው ገቢ መሠረት ስርጭቱን በ4 ዙር ለማከናወን የታቀደ ሲሆን በመጀመሪያው ዙር በትግራይ 7 ሀገረ ስብከቶች ውስጥ ለሚገኙ 50 አድባራትና ገዳማት እንዲሁም አብያተ ክርስቲያናት ለአንድ ዓመት የሚሆን የመብዐ ስጦታ ተሰጥቷል፡፡

 

ስጦታው የተከፋፈለው ለአንድ ሳምንት የቆየ ጉዞ በማከናወን በየአድባራቱና ገዳማቱ በመገኘት ሲሆን ስርጭቱ ካካተታቸው ሀገረ ስብከቶች መካከል በደቡብ ትግራይ አርማጭሆ፤ እንደርታ፤ አዲግራት፣ አክሱም፣ ሽሬና ሁመራ ይገኙበታል፡፡ ከገዳማቱ መካከል ደብረ ሳሙኤል ዘሃሌ ሉያ፣ ደብረ በንኮል አቡነ መድኀኒነ እግዚእ፤ አባ ዮሃኒ ዘቆላ ተንቤን፣ አባ ቶማስ ዘደብረ ማርያም ዘሃይዳ፣ ፀአዳ አምባ አቡነ መርአዊ ክርስቶስ፣ እንደቆርቆር ቅድስት ማርያም ገዳማት ይገኙበታል፡፡

አድባራቱና ገዳማቱ ሰው የማይደርስባቸው ሊባሉ የሚችሉ በረሃማና ጠረፋማ አካባቢዎች ሲሆኑ እቅዱን ለማሳካት አስፋልቱንና ኮረኮንቹንYeMeba Serechet በመኪና፤ ተራራውንና ተዳፋቱን በግመል በመጫንና በማከፋፈል ምንም መቀደሻ እጣን፣ ጧፍ፣ ዘቢብ እንዲሁም ልብሰ ተክህኖ ለሌላቸው ለማዳረስ ከፍተኛ ጥረት ተደርጓል፡፡ ስርጭቱን የተቀላጠፈ ለማድረግ በየሀገረ ስብከቱ የሚገኙ የማኅበሩ ማእከላት አባላት ድርሻ ከፍተኛ ነበር፡፡

 

በስጦታው ወቅት አባቶች ያሉባቸውን የመብዐ እጥረት ገልጸው “ዛሬ ዐይናችን እንደበራ እንቆጥረዋለን” በማለት የተደረገላቸውን ስጦታ ውዳሴ ማርያም እየደገሙና የኪዳን ጸሎት እያደረሱ መብዐውን ለሰጡ ምእመናንና ማኅበረ ቅዱሳን በጸሎት በማሰብ ተቀብለዋል፡፡

 

በተያያዘም በዋነኛነት ትኩረት ከተደረገባቸው ገዳማት ውስጥ ትግራይ ፀአዳ አምባ አቡነ መርአዊ ክርስቶስ ገዳም ይገኝበታል፡፡ ታላላቅ አባቶችን ያፈራ ገዳም እንደሆነና በረሃብና እርዛት፤ እንዲሁም ሆድ በሚነፋ በሽታ ምክንያት አባቶች በችግር ላይ እንደሚገኙ የተገለጸ ሲሆን እውነታውን በፊልም በማስደገፍ ለምእመናን ቀርቧል፡፡ በሽታው በጥናት ሊደረስበት እንዳልተቻለ መነኮሳቱ የሚገልፁ ሲሆን የአካባቢው ምእመናን በበሽታው ምክንያት ወደ ሰፈራ በመሄዳቸው ገዳማውያኑ ብቻቸውን ቀርተዋል፡፡ ከገዳሙ የሁለት ሰዓት የእግር ጉዞ በኋላ የእርሻ ቦታ ያላቸው ቢሆንም የገዳሙ አባቶች በእርጅናና በጤና መታወክ ሳቢያ ማረስ አልቻሉም፡፡ ከዚህ ቀደም የአካባቢው ምእመናን ያርሱላቸው እንደነበር ተናግረዋል፡፡ “አበው ያቆዩልንን ቅርስና ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን ጥለን አንሄድም” በማለት ጸንተው ቆይተዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት 52 መነኮሳት ብቻ የሚገኙ ሲሆን በአልባሳትና በምግብ እጥረት እየተሰቃዩ ይገኛሉ፡፡ በዚህም ምክንያት የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ትኩረት አድርጎ ለእነዚህ አባቶች ምእመናን እንዲደርሱላቸው ጥረት በማድረግ ላይ እንደሚገኝ ተገልጿል፡፡ እስከ ነሐሴ 2004 ዓ.ም. ድረስ ለአልባሳት 15.600 ብር እንዲሁም ለቀለብ 20.800 ብር እንደሚያስፈልግ በመርሐ ግብሩ ወቅት በመገለጹ በእለቱ ከተገኙ 2 በጎ አድራጊ ምእመናን ከላይ የተጠቀሱትን ወጪዎች እንደሚሸፍኑ ቃል ገብተዋል፡፡ ዋና ክፍሉም ምስጋናውን በማቅረብ ምእመናን ድጋፋቸውን እንዳይለይ አጽንኦት በመስጠት “እናንተ ሁል ጊዜ ስጡ፣ ከቅዱሳን በረከትን ታገኛላችሁ፣ እጃችሁ ከምጽዋት አይጠር፣ እኛም አደራችሁን ተቀብለን አገልግሎት ለመስጠት ዝግጁ ነን” በማለት የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት የቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ መሠረት ገልጸዋል፡፡

 

በዜና ገዳማት ወርሐዊ መርሐ ግብር ከተዳሰሱት መካከል ለዝቋላ ገዳም በቃጠሎው ምክንያት ጊዜያዊ ድጋፍና የፕሮጀክት ጥናት መደረጉ ተገልጿል፡፡ በቃጠሎው ወቅት የቀለብ እጥረት በመከሰቱ ማኅበረ ቅዱሳን ምእመናንን በማስተባበር 50 ኩንታል ስንዴ፣ 20 ኩንታል ጤፍ፣ 40 ሺህ ብር የሚገመት ውኃ፣ በሶ፣ ስኳርና ዳቦ ድጋፍ ተደርጓል፡፡ በተጨማሪም በሰሜን አሜሪካ የሚገኙ ከማኅበረ ቅዱሳን አባላትና ከበጎ አድራጊ ምእመናን የተሰበሰበ ለድጋፍ የሚሆን 125 ሺህ ብር ተሰብስቧል፡፡ ወደ ዝቋላ ገዳም ባለሙያዎችን በመላክ ለገዳሙ የሚሆን የእርሻ ቦታ፣ የመጠጥ ውኃና የመንገድ ችግሮችን ለመቅረፍ የሚያስችል ጥናት ተደርጓል፡፡ የደብረ ዘይት ማእከል አባላት የዝቋላን ገዳም አስቸጋሪ መንገድ ለመጠገንና ለማስተካከል ምእመናንን በማስተባበር ከፍተኛ ርብርብ ላይ እንደሚገኙ በሪፖርቱ ተገልጿል፡፡ የጎንደር ወደብረ ጥበባት በዓታ ለማርያም ገዳም የአብነት ተማሪዎች ማደሪያ ቤት ግንባታ መጀመሩም በሪፖርቱ ከተካተቱት አበይት ክንውኖች አንዱ ሆኗል፡፡

 

በቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ዳይሬክተር በዲ/ን አእምሮ ይሄይስ በክፍሉ የተከናወኑ ፕሮጀክቶችን አስመልክቶ የ10 ዓመት ሪፖርት አቅርበዋል፡፡ በሪፖታቸውም በእርሻ ፤ንብ ማነብ፤ግንባታ፤ የወተት ላምና ከብት ማድለብ እንዲሁም ሰው ኃይል ማፍራት ላይ ያተኮሩ ፕሮጀክቶች ተሠርተዋል፡፡ ከፕሮጀክቶቹ መካከል በአብዛኛው የአብነት ትምህርት ቤት ግንባታ፣ የመምህራንና የተማሪዎች መኖሪያ፤ የጉባኤ ቤትና የካህናት ማሠልጠኛ፣ የካህናትና መነኮሳት መኖሪያ ግንባታ ፕሮጀክቶች ሰፊውን ድርሻ እንደሚይዙ በስፋት አብራርተዋል፡፡ በጥናት ላይ የሚገኙ ፕሮጀክቶች በሂደት ላይ ሲሆኑ ከእቅድ ውጪም እየተከናወኑ ያሉ ፕሮጀክቶች ይገኛሉ፡፡በተጨማሪም 145 የአብነት ትምህርት ቤቶች፣ 136 መምህራን፤ 865 ተማሪዎች በየወሩ እየተደጎሙ እንደሚገኙ ዲ/ን አእምሮ ይሔይስ ገልጸዋል፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ላይ በዲ/ን ብርሃኑ አድማስ ትምህርተ ወንጌል የተሰጠ ሲሆን የ3 ወራት የሒሳብ ሪፓርት ቀርቧል፡፡ ከምእመናን በክፍሉ እንቅስቃሴና በገዳማት ዙሪያ አስተያየት ተሰጥቷል፡፡ ከ800 በላይ ጥሪ የተደረገላቸው በመብዐ ሳምንት ድጋፍ ያደረጉ ምእመናንና በጎ አድራጊዎች በመርሐ ግብሩ ላይ ተሳትፈዋል፡፡

 

ዜና ገዳማት በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል በየወሩ እየተዘጋጀ የገዳማትንና አድባራትን ነባራዊ ሁኔታ፣ የክፍሉን እቅዶችና ተግባሮች እንዲሁም የተተገበሩና በዝግጅት ላይ ያሉ ፕሮጀክቶች የሚተዋወቁበት መርሐ ግብር መሆኑ ይታወቃል፡፡

የእግር ጉዞው ምዝገባ ሊጠናቀቅ ቀናት ቀሩት

ግንቦት 16/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

{gallery count=1 width=350 height=300 counter=1 links=0 alignment=center animation=3000}yeger guzo{/gallery}

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የማኅበረ ቅዱሳን 20ኛ ዓመት ምሥረታን ምክንያት በማድረግ “ለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት አብረን እንሥራ” በሚል መሪ ቃል ግንቦት 26 ቀን 2004 ዓ.ም. የእግር ጉዞ መዘጋጀቱ ይታወቃል፡፡ የመርሐ ግብሩ ዐቢይ ኮሚቴ አስተባባሪ ዲ/ን ዋሲሁን በላይ የእግር ጉዞው ምዝገባ በፍጥነት እየተካሔደ መሆኑንና በርካታ ቲኬቶችና ካናቴራዎች በመሠራጨት ላይ እንደሚገኙ እንዲሁም ሊጠናቀቅ ቀናት እንደ ቀሩት ገልጸዋል፡፡

 

ዲ/ን ዋሲሁን በላይ ለምእመናን ባስተላለፉት መልእክት፡- “ዋናው የጉዞው ዓላማ የማኅበራችን 20ኛ ዓመት ምሥረታ ነው፡፡ በ20 ዓመታት ውስጥ ማኅበረ ቅዱሳን ብቻውን የፈጸመው የቤተ ክርስቲያን አገለግሎት የለም፡፡ ከቅዱስ ፓትርያርኩ ጀምሮ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ከቤተ ክርስቲያኒቱ የተለያዩ አካላትና ጽ/ቤቶች፣ ከሠራተኛ ጉባኤያት ከሰንበት ትምህርት ቤቶች በተለይም ከምእመናን ጋር በኅብረት ሠርተናል፡፡ አብረን ከተጓዝናቸው፣ እስካሁንም ደከመን ሰለቸን ሳይሉ በምክራቸው በጸሎታቸው በእውቀታቸው፣ በገንዘባቸውና በጉልበታቸው እያገለገሉ ካሉ አካላትና ምእመናን ጋር በኅብረት እግዚአብሔርን የምናመሰግንበት ቀን ነው፡፡ ቀጣይ ጊዜያችን ደግሞ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ጠንክረን አብረን ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከእኛ የምትፈልገውን አገልግሎት የምንፈጽምበት እንዲሆን ቃል የምንገባበት ዕለት ነው፡፡” በማለት የገለጹ ሲሆን ምእመናን የተዘጋጀውን ቲኬት በመግዛት በእግር ጉዞው እንዲሳተፉና የበረከቱ ተሳታፊ እንዲሆኑ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

አንዳንድ ምእመናን እንደሚገልጹት ጉዞው ማኅበረ ቅዱሳን ከዚህ በኋላ ላሉት የአገልግሎት ዘመናት ዘመኑን የዋጅና እየመጣ ያለውን የትውልዱን አስተሳሰብና የአኗኗር ለውጥ ማዕከል ያደረገ አገልግሎት እንዲያበረክት ድልድይ እንደሚሆነው ይገልጻሉ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ከሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ወጥቶ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ ሥር እንዲመራ ቅዱስ ሲኖዶስ ወሰነ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ከሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ወጥቶ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ ሥር እንዲመራ ቅዱስ ሲኖዶስ ወሰነ፡፡
በዓመት ሁለት ጊዜ የሚካሄደው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የዘንድሮውን መደበኛ የርክበ ካህናት ስብሰባ በልዩ ልዩ የአጀንዳ ነጥቦች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ በማሳለፍ ተጠናቀቀ፡፡ ከጉባኤው መጠናቀቅ በኋላ ውሳኔዎቹን በተመለከተ ከልዩ ልዩ የመገናኛ ብዙሃን ለተወከሉ ጋዜጠኞች መግለጫ የሰጠው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ማኅበረ ቅዱሳን ከሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ወጥቶ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ ሥር እንዲመራ ወስኗል፡፡ የቤተ ክርስቲያኗን ትምህርት በማዛባት የኑፋቄ ትምህርት ሲያስተላልፉ የተገኙ የተሐድሶ መናፍቃንም ተወግዘዋል፡፡
ሚያዝያ 30 ቀን 2004 ዓ.ም. የመክፈቻ ጸሎት አድርጎ እስከ ግንቦት 15 ቀን በተደረገው ጉባዔ ያሳለፋቸውን ውሳኔዎች ይህን በመጫን ያንብቡ፡፡

ግንቦት 15/2004 ዓ.ም.

 

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖአምላክ

በዓመት ሁለት ጊዜ የሚካሄደው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የዘንድሮውን መደበኛ የርክበ ካህናት ስብሰባ በልዩ ልዩ የአጀንዳ ነጥቦች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ በማሳለፍ ተጠናቀቀ፡፡ ከጉባኤው መጠናቀቅ በኋላ ውሳኔዎቹን በተመለከተ ከልዩ ልዩ የመገናኛ ብዙሃን ለተወከሉ ጋዜጠኞች መግለጫ የሰጠው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ማኅበረ ቅዱሳን ከሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ወጥቶ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ ሥር እንዲመራ ወስኗል፡፡ የቤተ ክርስቲያኗን ትምህርት በማዛባት የኑፋቄ ትምህርት ሲያስተላልፉ የተገኙ የተሐድሶ መናፍቃንም ተወግዘዋል፡፡

ሚያዝያ 30 ቀን 2004 ዓ.ም. የመክፈቻ ጸሎት አድርጎ እስከ ግንቦት 15 ቀን በተደረገው ጉባዔ ያሳለፋቸውን ውሳኔዎች ይህን በመጫን ያንብቡ ፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስን መግለጫ ከዚህ ይመልከቱ፡፡

ሰበር ዜና

 

ግንቦት 15/2004 ዓ.ም.

ማኅበር ቅዱሳን በቤተ ክህነት ጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ እንዲመራ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ወሰነ፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስን መግለጫ ከዚህ ይመልከቱ፡፡

ዝርዝሩን እንደደረሰን እናቀርባለን፡፡

በዋልድባ ገዳምና በወልቃይት ስኳር ልማት ፕሮጀክት መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት አስመልክቶ ማኅበረ ቅዱሳን ያደረገው ጥናት ዘገባ

 

ግንቦት 10/2004 ዓ.ም.

ካለፉት ሁለትና ሦስት ወራት ወዲህ ከዋልድባ ገዳም ጋር በተያያዘ በመንግሥትና በገዳሙ መካከል አለመግባባት ተከስቷል፡፡ አለመግባባቱም ብዙዎችን አነጋግሯል፣ አከራክሯል፡፡ ከጉዳዩ መግዘፍ የተነሣ በርካቶችን ሲያስጨንቅና ሲያሳስብ ቆይቷል፡፡ የበርካታ ኢትዮጵውያንን ትኩረት የሳበ ሀገራዊ ጉዳይም ሆኗል፡፡ አለመግባባቱን ለማወቅ ከመጓጓት አንጻርም፤ የጉዳዩን ምንጭና መፍትሔ ነጣጥሎ ማየት እስከ ሚከብድ ድረስ በሰው ልቡና ሲመላለስ ቆይቷል፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳንም እውነታውን ለማጣራት ከመጋቢት 25-30 ቀን 2004ዓ.ም አምስት አባላት ያሉት የልዑካን ቡድን ወደቦታው ልኮ ነበር፡፡ ቡድኑ በቦታው በመገኘት ሁሉንም አካላት ማለትም የገዳሙን አባቶች (የገዳሙ አባቶች ስማቸው እንዲጠቀስ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው፤ በጽሑፉ ውስጥ የገዳሙ መነኮሳት በሚል የወል ስም ተገልጸዋል)፣ የፕሮጀክቱን ሓላፊዎች፣ የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች በማነጋገር ያገኘውን ምላሽ ከልዑካኑ ዕይታ ጋር በመጨመር ሰፋ ያለ ሪፖርት ይዞ ተመልሷል፡፡ የዚህ ጽሑፍ ዓላማ የልዑኩን ሪፖርት የማኅበሩ አመራር አካል ከሰማ በኋላ፤ ከልዩ ልዩ አቅጣጫዎችና ተጨማሪ መረጃዎች ጋር በመመርመር ያጸደቀውን ሪፖርት ማቅረብ ነው፡፡

 

m.gerema

“ዝክረ ገብረ እግዚአብሔር” በሚል ርዕስ ጉባኤ ተካሄደ፡፡

ግንቦት 10/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖአምላክ

m.gerema በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ደብረ አሚን ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን የምክሐ ደናግል ማርያም ወጣቶች መንፈሳዊ ማኅበር (ሰንበት ት/ቤት)  ያዘጋጀውና መ/ር ግርማ ከበደ በዚህች ዓለም ሳለ ያስተማራቸው ልዩ ልዩ ትምህርቶችን አሰባስቦ የያዘው  ሲዲ የተመረቀው ሚያዚያ 27 ቀን 2004 ዓ.ም. ነበር፡፡

 

“ዝክረ ገብረ እግዚአብሔር” በሚል ርእስ በተካሄደው በዚሁ ጉባኤ ላይ መምህር ግርማ ከበደ በዚህ ዓለም ሳለ ያስተማራቸው ትምህርቶችና የሰበካቸው ስብከቶች በአንድነት ተሰባስበው /በMP3 ፎርማት ተዘጋጅተው/ በሲዲ ለምእመናን ተሰራጭተዋል፡፡

 

በደ/አሚን ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን የምክሐ ደናግል ማርያም ወጣቶች መንፈሳዊ ማኅበር / ሰንበት ትምህርት ቤት/ ም/ሰብሳቢ ወጣት አበበ ተሻለ ይህን የትምህርት ሲዲ ለማዘጋጀት የታሰበበትን ምክንያት ሲያስረዳ፡- “ጋሽ ግርማ ያስተማራቸውን ትምህርቶችና የሰበካቸውን ስብከቶች ከማሰባሰብ ጀምሮ በየደረጃ የሚሠሩትን ሥራዎች በማጠናቀቅ፣ ሳይገባን፣ በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በጻድቁ አባታችን ተክለ ሃይማኖት ጸሎት ለሃይማኖት ቤተሰቦቹ ስናቀርብ ታላቅ መንፈሳዊ ደስታ ይሰማናል፡፡ይህንን ሲዲ ለማዘጋጀት  ምክንያት የሆነን፡- ምእመናን  በልዩ በልዩ ጊዜያት  በሰ/ት/ቤታችን የሚገኙ የጋሽ ግርማ ትምህርቶችን በማባዛት እንድናሰራጭ ስለጠየቁን፤ በተጨማሪም በአሁኑ ወቅት ረሃበ ነፍስ የተባለው የቀና ሃይማኖትና በጎ ምግባር ማጣት እየተስፋፋ በመምጣቱ የጋሸ ግርማ ስብከቶች እነዚህን ትልልቅ ችግሮች ይቀርፋሉ ብለን በማመናችን ነው፡፡ በሌላ በኩል፡- ጋሽ ግርማ አብዛኛው ሰው በልቡ የሚነሣበትን ጥያቄ በትምህርቱ ከመመለሱ በላይ ፈተናም ያርቅ ነበርና….. እኛ የሰማነውን ሌሎችም ቢሰሙ ሊጠቀሙ እንደሚችሉ በማመን ልናዘጋጀው ችለናል፤” ብሏል፡፡

 

yo 3ወጣት አበበ በዚሁ ሪፖርቱ ማጠናቀቂያ ላይ ሰንበት ትምህርት ቤቱ በቀጣይ ስለሚፈጽመው አገልግሎት ሲያስተዋወቅ “ከጋሽ ግርማ የተማርንም ሆንን በስም የምናውቀው ድምፁን መስማታችን በራሱ ያስደስተናል በሚል እምነት ለጊዜው ሦስት ሲዲዎችን አዘጋጅተናል፡፡ በቀጣይ ዝግጅታችን “በምሥጢረ ሥላሴ፣ በምሥጢረ ሥጋዌ፣ በምሥጢረ ጥምቀትና በምሥጢረ ትንሣኤ ሙታን እንዲሁም በሌሎች ተጓዳኝ ርእሶች ያስተማራቸውን ትምህርቶችና የሰበካቸውን ስብከቶች እንድናቀርብ ጸሎታችሁ አይለየን” በማለት ምእመናንን አሳስቧል፡፡

 

በምክሐ ደናግል ማርያም ሰንበት ትምህርት ቤት አባልና የ˝ዝክረ ገብረ እግዚአብሔር” ጉባኤ አስተባባሪ የሆኑት መ/ር ዮሐንስ አየለን “የጋሽ ግርማን ትምህርቶች በመጽሐፍ መልክ ለማዘጋጀት ምን የታሰበ ነገር አለ?” በሚል ላቀረብንላቸው ጥያቄ ምላሽ ሲሰጡ፡- “…የጋሽ ግርማን ሕይወት አስመልክቶ ዘጋቢ ፊልም ለመሥራት ቃለ መጠይቅ ያደረግንላቸው ወገኖች ጋሽ ግርማ በመቅረጸ ድምጽ ወምስል ያልተያዙ በርካታ ትምህርቶቹ በማስታወሻ ደብተሮቻቸው እንደሚገኝ ገልጸውልን፣ በመጽሐፍ መልክ አዘጋጅታችሁ ብታወጧቸው በማለት ትውልዱ ይማርባቸው ይመከርባቸው ዘንድ ትምህርቱን የዘገቡባቸውን ማስታወሻ ደብተሮቻቸውን ሰጥተውናል፡፡ ይህንኑ ዐሳብ ኮሚቴው ተቀብሎ የሰንበት ትምህርት ቤታችን ጽሕፈት ቤት በፕሮግራሙ ውስጥ አካቶ ይዞታል፡፡ ለዚህም እንዲረዳ በአሁኑ ወቅት በሲዲ የቀረቡት ሰላሳ ስድስቱም   ትምህርቶች ቃል በቃል ወደ ጽሑፍ ተቀይረዋል፡፡ በቀጣይም  አስፈላጊው ማስተካከያ ተደርጎለት ለመጽሐፍ በሚሆን መልኩ የማዘጋጀት ተግባር ይከናወናል፡፡” ብለውናል፡፡

 

በሌላ በኩል በጋሽ ግርማ ትምህርቶች አማካኝነት ስለሆኑ ድንቅ ነገራት የጠየቅናቸው መ/ር ዮሐንስ፡- “በመቀሌ ቢዝነስ ኮሌጅ ተማሪ የነበረ አንድ ወንድማችን የመምህር ግርማ ከበደን ትምህርት የያዘ አጀንዳ አግኝቶ ወደ ራሱ ማስታወሻ መገልበጥ ይጀምራል፡፡ ሆኖም ይህን ሥራ እያከናወነ ሳለ አንድ ሌሊት ላይ ተኝቶ ሕልም አየ ይኸውም በመሐል ክንዱ ርግብ አርፋ ስትጠረጥረው /በአፏ ስትቧጭረው/ ያያል፡፡ ከሁለት ቀን በኋላ ያ ቦታ ያብጥበታል፡፡ መጻፍም አልቻለም፡፡ በኋላ መቀሌ በዓታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ የነበሩ መልአከ ስብሐት አባ አብርሃም ዘንድ ሄደን ልጁ ስላየው ነገርና ስለገጠመው ሁኔታ ስንነግራቸው “መምህሩ (ጋሽ ግርማን ነው) የተጠቀመ ነው፡፡ በትሩፋት በገድል ነው የሚያስተምረው” አሉን፡፡ ከዚህ በኋላ ልጁ ትምህርቱን አቋርጦ ወደ አዲስ አበባ መጣ፡፡ በአዲስ አበባ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ምርመራ ያደረጉለት የጤና ባለሙያዎችም፤ እጁ መቆረጥ እንዳለበት ያለዚያ ለደኅንነቱ አስቸጋሪ እንደሚሆንበት ነገሩት፡፡ በሰማው ነገር እጅግ ተደናግጦና አዝኖ መጥቶ አጫወተን፡፡ መምህራንን ስናማክር ለጻድቁ ተክለሃይማኖት እንዲለምን እንዲሳል ተነገረው፡፡ ልጁም  በደብረ አሚን ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን መቅደስ መግቢያ ላይ የሚገኘውን የቅዱስ ተክለሃይማኖት ስዕል ሥር ቀርቦ ተማጸነ፡፡ ጸሎቱን አድርሶ የመሬቱን ትቢያ አንስቶ ከታመመበት እጁ ላይ ቀባባው፡፡ ይህ ከሆነ ሦስት ቀን ሳይሞላው እብጠቱ ሙሉ ለሙሉ ጎደለለት፡፡ ይህንኑ ነገር ለመልአከ ስብሐት አብርሃ /የመቀሌ እንዳ ማርያም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ/ ነገርናቸው፡፡ እርሳቸውም “ይህ መምህር በገድል በትሩፋት የሚያስተምር ነው፡፡ ስለሆነም የበጎ ነገር ሁሉ ተጻራሪ የሆነ ጠላት ዲያብሎስ ትምህርቱ እንዳይወጣ ሰው እንዳይጠቀም ሲፈታተን ነው፤” አሉን፡፡

 

በሌላ ጊዜም “በይሖዋ ምስክር እምነት ውስጥ የነበረች አንዲት አህት የቤተክርስቲያንን ትምህርት መማር ትፈልጋለችና መጥታችሁ አነጋግሩልን” በሚል ከቤተሰቦቿ ለሰንበት ትምህርት ቤታችን ልጆች መልእክት ይመጣል፡፡ በዚህ ጊዜ ሁለት አባላት ወደ ልጅቱ ቤት ይሄዳሉ፡፡ ነገር ግን ከአንድም ሁለት ጊዜ ወንድሞች ሲሄዱ ለመማር ፈቃደኛ አልነበረችም፡፡ በሌላ ጊዜ ከቤተ ክርስቲያን የማትለይ እህቷ የትምህርት ካሴት ይዛ ወደ ቤቷ ትሄዳለች፡፡ ያንኑ ትምህርትም ከፍታ ልጅቱ ትተኛለች፡፡ በቤታቸው የሚገኘውም የካሴት ማጫወቻ ቴፕ ሰው ካላጠፋው በቀር በራሱ አያቆምም፡፡ በካሴቱ የተቀረጸው ትምህርት ጋሽ ግርማ በዚህ ዓለም ሳለ፡- ˝በእኔ የማይሰናከል ብጹእ ነው” ሲል ጌታችን የተናገረውን ቃል ያስተማረበት ነው፡፡ ፈቃደ እግዚአብሔር ሆኖ በይሖዋ ምስክር ቤተ እምነት ውስጥ የነበረችው ልጅ ከእንቅልፏ ነቅታ ታናሽ እኅቷ የከፈተችውን የካሴት ትምህርት መስማት ጀመረች፡፡ ትምህርቱ “ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክ መሆኑን የሚገልጽ ነው፡፡ እናም ትምህርቱ በክኅደት በኑፋቄ የሸፈተ ልቡናዋን ወደ ሃይማኖት መልሰው፡፡ በጧት ተነስታ እናቷንና እኅቷን፡- ˝እነዚያን የቤተ ክርስቲያን ልጆች ማግኘት እፈልጋለሁ ጥሩልኝ” ትላለች፡፡ ልጆቹ ግን ለመከራከር ፈልጋ ነው እንጂ፤ ትምህርቱን በመሻት አይደለም በሚል ለመሄድ አመናቱ፡፡ ነገር ግን በሌላ ጉዳይ ነው የምትፈለጉት ተብለው ሲሄዱ ልጅቱ፡- ˝ይህንን ትምህርት ያስተማረው መምህር ማግኘት መተዋወቅ ከእርሱም መማር እፈልጋለሁ” ትላቸዋለች፡፡ ያን ጊዜ ግን ጋሽ ግርማ በሕይወት አልነበረም፡፡ ከዚህ በኋላ ˝ለካ እኔም በአምላኬ ቃል ተሰናክዬ ፈጣሪዬን ክጄ ኖሬያለሁ” በማለት ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በንስሐ ለመመለስ በቅታለች፡፡” እነኚህ ብቻ አይደሉም፡፡ እርሱ ያስተማረውን ትምህርት ሰምተው ንስሐ የገቡ፤ ሥጋ ወደሙ የተቀበሉ፤ ከክህደት ከነፋቄ ወደ ሃይማኖት የተመለሱ በርካቶች ናቸው” በማለት ነግረውናል፡፡

 

የትምህርቱን ሲዲ አዘጋጅቶ ለምእመናን ለማድረስ አንድ ዓመት ከስድስት ወር መውሰዱን የገለጹት መ/ር ዮሐንስ አየለ “በዝክረ ገብረ እግዚአብሔር መርሐ ግብር ላይ የተገኙ አንድ ምእመን የጋሽ ግርማን ኦሪጅናል የትምህርት ካሴቶች እንደሚሰጡን ቃል የገቡልን በመሆኑ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ቀጣዩ ሥራ ከአሁኑ የተሻለ ጥራት ይኖረዋል” ሲሉ ተናግረዋል፡፡

 

“ያመዋል፤ ነገር ግን ደዌ ባልተለየው ጊዜ እንኳ ሲያስተምር /ሲያገለግል/ ፈገግታ አይለየውም፡፡ ገድለ ገብረ መንፈስ ቅዱስን ሲያነብ ሲያስተምር በእንባ ጭምር ነው፡፡….”  በሚል ስለ ጋሽyo 1 ግርማ ምስክርነታቸውን ለጉባኤው የሰጡት መምህር (ጋሽ) ታዬ አብርሃም ˝ግርማ ምንም ያክል ቢሠራ ‘ይህን ሠራሁ፥ ይህን አደረግሁ’ በማለት አይናገርም፡፡ ውዳሴ ከንቱን አጥብቆ ይጠላል፡፡” በማለት ተናግረዋል፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙ አንዳንድ ምእመናን በሰጡት አስተያየት “ ስለጋሽ ግርማ መታሰቢያ ስንነጋገር፤ እርሱ በፈቃደ እግዚአብሔር ማስተማር የጀመረበት ጉባኤ እንዳይፈታ የየራሳችንን አስተዋጽኦ እናበርክት፡፡”

 

ሌላው አስተያየት ሰጪ ምእመን እንዲህ ሲሉ ተናግረዋል፡- “በሕይወቴ ለውጥ እንዳይ የረዳኝ ጋሽ ግርማ ነው፡፡ ጋሽ ግርማ አሁን ላለው ስብእናዬ ከፈጣሪ በታች መሠረት የሆነኝ እርሱ ነው፡፡ የጋሽ ግርማ ስብከቱ ልዩ ነው፡፡ ስለሰው የሚገደው ሰው ነው፡፡ በእንባ ጭምር የሚያስተምር መምህር ነው፡፡…”

 

በመርሐ ግብሩ ማጠናቀቂያ ላይ የደብረ አሚን ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ መልአከ አሚን ሊቀ ጉባኤ ኤርሚያስ ወልደየሱስ  የትምህርት ሲዲውን መርቀው ለምእመናን በይፋ መታደሉን አብስረዋል፡፡

 

በክፍል አንድ ክፍል ሁለትና ክፍል ሦስት ሲዲዎች በአጠቃላይ ሰላሳ ስድስት ትምህርቶች የሚገኙ ሲሆን፤ በክፍል አንድና ሦስት የሃይማኖት ትምህርቶች እንዲሁም በክፍል ሁለት ላይ በልዩ ልዩ ርእሶች መምህር ግርማ የሰበካቸው ስብከቶች ተካተውበታል፡፡

የቅዱስ ያሬድ መታሰቢያ ዐውደ ርዕይ ተከፈተ

ግንቦት 8/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

 

ቅዱስ ያሬድ የተሠወረበትን መታሰቢያ ዓመት ምክንያት በማድረግ ከግንቦት 5-12 ቀን 2004 ዓ.ም. የሚቆይ ዐውደ ርዕይ አዲስ አበባ በሚገኘው ደብረ ይባቤ ቅዱስ ያሬድ ቤተ ክርስቲያን ተዘጋጀ፡፡ የቅዱስ ያሬድ 1500ኛ ዓመት የልደት በዓል በተለያዩ መንፈሳዊ መርሐ ግብሮች በደማቅ ሁኔታ በሚቀጥለው ዓመት ለማክበር የደብሩ አስተደደር የደብሩ ስብከተ ወንጌል ጽ/ቤት ሰበካ ጉባኤውና ሰንበት ትምህርት ቤቱ ተቀናጅተው እየሠሩ የሚገኙ ሲሆን ይህ አውደ ርዕይ የመርሐ ግብሩ አንድ አካል መሆኑን አዘጋጆቹ ገልጸዋል፡፡

ዓውደ ርዕዩ ካካተታቸው ዋና ዋና ጉዳዮች መካከል

  1. የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልዕኮ
  2. ቅዱሳት ስዕላት
  3. ዝክረ ቅዱስ የሬድ
  4. የሰንበት ትምህርት ቤት አገልግሎት በቤተ ክርስትያን የሚሉ ይገኙበታል፡፡

 

ግንቦት 5 ቀን 2004 ዓ.ም. ከቅዳሴ በኋላ በተከናወነው የአውደ ርዕይ መክፈቻ መርሐ ግብር ላይ የደብሩ አስተዳደር፤ የደብሩ ሰበካ ጉባኤ፣ የስብከተ ወንጌል ጽ/ቤትና የደብሩ ሰንበት ትምህርት ቤት አባላት እንዲሁም ምዕመናን በተገኙበት በድምቀት ተከፍቷል፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን አባቶችና የሰንበት ትምህርት ቤቱ አባላት ያሬዳዊ ዝማሬ አቅርበዋል፡፡ በመጨረሻም የአውደ ርእዩ አዘጋጆች የሆኑት የሰንበት ት/ቤቱና የስብከተ ወንጌል ጽ/ቤቶች ምእመናን በቤተክርስቲያኑ ተገኝተው ለአንድ ሳምንት የሚቆየውን አውደ ርእይ እንዲመለከቱ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

የአሰቦት ገዳምን ለመርዳት ጉባኤ ሊካሄድ ነው፡፡

ግንቦት 8/2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

የአሰቦት ደብረ ወገግ ቅድስት ሥላሴና አቡነ ሳሙኤል ገዳምን ለመርዳት ታላቅ መንፈሳዊ ጉባኤ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሸ ሰኔ 3 ቀን 2004 ዓ.ም. ከቀኑ 7 ሰዓት ጀምሮ ይካሄዳል፡፡ ከ800 ዓመታት በላይ እድሜ ያስቆጠረው ገዳም በፃድቁ አቡነ ሳሙኤል ዘደብረ ወገግ የተመሠረተ ሲሆን በቅርቡ የገዳሙ ደን  ተቃጥሎ ከፍተኛ ጉዳት የደረሰበት መሆኑ ይታወሳል፡፡

ገዳሙ ከከተማው 18 ኪ. ሜትር ርቀት ላይ የሚገኝ ሲሆን ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ለመድረስ 6 ኪሎ ሜትር ርቀት ያለውን ተራራ በእግር መውጣት ይጠበቃል፡፡ የመንገዱ አስቸጋሪነት ገዳሙን የልማት ተጠቃሚ ለማድረግ ያላስቻለው ሲሆን መንገዱን ለመሥራት ኮሚቴ በማዋቀር እንቅስቃሴ ተጀምሯል፡፡ ምዕመናን ይህንን ጥንታዊና ታሪካዊ ገዳምን ለመርዳት ትኬቱን በመግዛት ክርስቲያናዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ የገዳሙ አስተዳደር ጥሪውን ያቀርባል፡፡

maderaja memreya letter

በሕገወጦች በጨለማ የተዘጋጀው ደብዳቤ ተበተነ፡፡

ግንቦት 7/2004 ዓ.ም.

ከጥቂት ቀናት በፊት ማኅበረ ቅዱሳን ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ማእከላዊ አስተዳደር ተገዥ ካለመሆን አልፎ የተቋሙን ሕልውና ወደ መፈታተን እንደ ደረሰ በማተት የሚከስ ደብዳቤ ለሕግ ተገዢ ባልሆኑ ግለሰቦች በጨለማ ተረቅቆ በመምሪያው ሓላፊ እንዲፈረም ተደርጎ ሊወጣ እንደ ነበር፤ ነገር ግን በመምሪያው ሓላፊው በቆሞስ መልአከ ጽዮን አባ ኅሩይ መታገዱን ገልጸን ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ እስከ አሁን ምክንያቱ ግልጽ ባልሆነ ሁኔታ “ፍጹም ሕገ ወጥ ድርጊት በሕጋዊዋና በእውነተኛዋ ቤተ ክርስቲያን መፈጸም የለበትም፤ ይቁም” ያሉትን የመመሪያ ሓላፊ አስተዳደሩ ከቦታቸው አንሥቷል፡፡ በምትካቸውም ከግብረ አበሮቻቸው ጋር በመሆን ደብዳቤውን በወቅቱ በተገለጠው ሁኔታ በማርቀቅ፣ እንዲፈረምና እንዲሠራጭ የሞት ሽረት ትግል ሲያደርጉ ከነበሩት ግለሰቦች አንዱ የሆኑትን መምህር ዕንቊ ባሕርይ ተከሥተን ሾሟል፡፡

ቆሞስ አባ ኅሩይ በመምሪያ ሓላፊነት ተመድበው ቦታውን ከያዙበት ጊዜ ጀምሮ በማኅበሩ መስተካከል አለባቸው በሚሏቸው ጉዳዮች ላይ ሁሉ የማኅበሩን አመራር አካላት እየሰበሰቡ መመሪያ ሲሰጡ፣ ማኅበሩም መመሪያዎችን እየተቀበለ ወደ ተግባር ሲለውጥ ቆይቷል፡፡ ቆሞስ አባ ኅሩይ ደብዳቤ በማርቀቅ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ልዩ ልዩ ክፍሎች አልፎ እስከ ብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን በሚደርስ ሁኔታ በማብረር የማያምኑ ውይይት ተኮር ዘመናዊ የአመራር ዘዴን የሚከተሉ በመሆናቸው ማኅበሩ መመሪያቸውን ሁሉ እየተቀበለ በማገልገል ላይ ነበር፡፡ ማኅበሩ የሚፈልገው በመጠነ ሰፊ ችግሮች ውስጥ ባለች ቤተ ክርስቲያን ሠርቶ የሚያሠራው ነውና፡፡

የመምሪያ ሓላፊው ቆሞስ አባ ኅሩይ ባላጠፉት ጥፋት ተከሰው ከቦታው መነሣታቸውን በመቃወም ለችግሩ መፍትሔ እንዲሰጥ ማኅበሩ ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ደብዳቤ ጽፏል፡፡ ጉዳዩም በቅዱስ ሲኖዶስ በአጀንዳነት ተይዟል፡፡

maderaja memreya letter

ማኅበሩ ለጻፈው ደብዳቤ ምላሽ በሚጠብቅበት በአሁኑ ወቅት፤ በመምሪያ ሓላፊነት የተመደቡት መምህር ዕንቊ ባሕርይ ተከሥተ ለረጅም ዓመታት የታገሉለትን ማኅበሩን የማደናቀፍ እኲይ ተግባር የሚያረጋግጡላቸውን ደብዳቤዎች ማብረር ጀምረዋል፡፡ በትላንትናው ዕለት ካበረሯቸው ደብዳቤዎች አንዱ ለቆሞስ አባ ኅሩይ መነሣት ምክንያት የሆነውንና ራሳቸው መምህር ዕንቊ ባሕርይ ከመሰል ግብረ አበሮቻቸው ጋር ሆነው አርቅቀው እንዲፈረምና እንዲበር የተሯሯጡለት ደብዳቤ ነው፡፡

 

የማኅበሩ አመራር በደብዳቤው ይዘትና በመምሪያችን እየተፈጠረ ስላለው የተጠናና ቤተ ክርስቲያኗን የማዳከም እንቅስቃሴ ላይ ውይይት በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ ጉዳዩን አስመልክቶ ለቅዱስ ሲኖዶስ ያቀረበውን አቤቱታ መልስ ይጠብቃል፡፡ በሒደቱ የሚፈጠሩትን ማናቸውንም ክስተቶች እየተከታተለ ለምእመናን ይፋ ያደርጋል፡፡

mk letter to synodos

የማኅበሩ አባላትም ሆኑ ምእመናን ዛሬ በማኅበራችን ላይ እየደረሰ ያለው ችግር በእናት ቤተ ክርስቲያን ላይ እየደረሰ ካለው ጋር ሲነጻጸር እዚህ ግባ የማይባል በመሆኑ አገልግሎታችንን በተለመደው ሁኔታ አጠናክረን እንድንቀጥል እናሳስባለን፡፡