ሌሎች መካነ ድሮች

Normal 0 false false false EN-US X-NONE TH MicrosoftInternetExplorer4


 

ጸሎትና ጥቅሙ

             

ልጆች ትምህርት ጥሩ ነው?ቤተ ክርስቲያን እሑድ እሑድ ትሔዳላችሁ ? በጣም ጥሩ ልጆች ! ዛሬ የምንማማረው ስለ ጸሎት ጥቅም ነው፡፡ ጸሎት ማለት ከእግዚአብሔር የምንገናኝበት እግዚአብሔርን የምናመሰግንበት ትልቅ ኃይል ማለት ነው፡፡

በጸሎት የእግዚአብሔርን ሩህሩህነት፣ ቸርነት ኃያልነት እንገልጻለን፡፡ በጸሎት እግዚአብሔር ያደረገልንን ሁሉ አስታውሰን ምስጋና እናቀርባለን፡፡  በጸሎት በደላችንን ለእግዚአብሔር እንናዘዛለን፡፡ ይቅርታውንም እንጠይቃለን፡፡ በጸሎት ከእግዚአብሔር የፈለግነውንና የጐደለንን ለማግኘት እንለምናለን፡፡ ጸሎት ይቅርታ መጠየቂያ በመሆኗ ከቅጣትና ከመከራ የምታድን ናት፡፡ እንግዲህ ልጆች በአጠቃላይ የጸሎት ጥቅም ተነግሮ የሚያልቅ አይደለም፡፡ ልጆች እናንተስ ጠዋት ከመኝታችሁ ስትነሡ ማታ ስትተኙ ትጸልያላችሁ ?
ወይንስ ዝም ብላችሁ ትተኛላችሁ፡፡ ትነሣላችሁ? ማታ ስትተኙ እግዚአብሔርን አመስግናችሁ ጠዋት ስትነሡ እግዚአብሔርን አመስግናችሁ ጸልያችሁ መዋል አለባችሁ፡፡ ልጆች ምግብም ስትመገቡ ጸሎት አድርሳችሁ መመገብ አለባችሁ፡፡ ልጆች ጸሎት ትምህርታችሁን ይገልጽላችኋል፡፡ ከብዙ ክፉ ነገር እግዚአብሔር ይጠብቃችኋል፡፡
እንግዲህ ልጆች ጸሎት ብዙ ዓይነት ነው፡፡ 1ኛ የግል ጸሎት፣ 2ኛ. የማኅበር ጸሎት 3ኛ. የቤተሰብ ጸሎት አለ፡፡ ስትጸልዩ በጸጥታና ካለወሬ መጸለይ ያስፈልጋችኋል፡፡ በአጠቃላይ የጸሎትን ጥቅም ማወቅ ይገባናል፡፡ እሺ ልጆች! ከብዙ በጥቂቱ የጸሎትን ጥቅም እንዳወቃችሁ ተስፋ እናደርጋለን፡፡

ሥነ ፍጥረት

ልጆች የምንነግራችሁ ስለ ሥነ ፍጥረት ነው፡፡ እግዚአብሔር የሚታየውን ዓለም የፈጠረው በስድስት ቀናት ውስጥ ነው፡፡ ይህም በአንድ ቀን ለመፍጠር አቅም አጥቶ አይደለም፡፡ እርሱ ባወቀ ሁሉን በሥርዐትና በአግባቡ ለማድረግ ብሎ ነው እንጂ፡፡ ደግሞም ፈቃዱና ጊዜውም ስለሆነ ፍጥረታትን በስድስት ቀናት ውስጥ አከናወነ፡፡ 

 
የዕለታት መጀመሪያ እሑድ ናት፡፡ እግዚአብሔር በዕለተ እሑድ በመጀመሪያው ቀን አራቱ ባሕርያት የተባሉትን መሬት፣ ውኃ፣ ነፋስ፣ እሳትን ፈጠረ፡፡ በሁለተኛዋ ዕለተ ሰኞ እግዚአብሔር ጠፈርን ፈጠረ፡፡
በሦስተኛው ቀን በዕለተ ማክሰኞ ልዑል እግዚአብሔር ምድርን፣ ዘርን የሚሰጥ ሣርንና ቡቃያን በምድርም ላይ እንደ ወገኑ ዘር ያለበትን ፍሬን የሚያፈራ ዛፍን ታብቅል ብሎ በዚያ መሬት፣ አትክልትን፣ አዝርዕትን፣ ዕፅዋትን አስገኘች /ዘፍ. 1፡12/ እነዚህ ከአራቱ ባሕርያት መካከል ከመሬት፣ ከውኃ፣ ከነፋስ ተፈጠሩ፡፡
ዓርብ በመጀመሪያው ሰዓት በመዓልት ልዑል እግዚአብሔር አዳምን ፈጠረው፡፡ ከአዳም በፊት የተፈጠሩት ፍጥረታት በሀልዮና በነቢብ የተፈጠሩ ሲሆን፤ እግዚአብሔር አዳምን የፈጠረው በእጆቹ በማበጃጀት ነው፡፡ እግዚአብሔር ሰውን ለመፍጠር ሰውን በመልካችንና በአርአያችን እንፍጠር አለ /ዘፍ. 1፡26/
በአራተኛው ቀን የረቡዕ ፍጥረት የሆኑት በሰማይ ጠፈር ብርሃን ይሁን ብሎ በቃል በማዘዝ ሦስቱን ፍጥረታት ፀሐይን፣ ጨረቃንና ከዋክብትን ፈጠራቸው፡፡ /ዘፍ.1፡14/ ሐሙስ ማለት አምስተኛ ዕለት ማለት ነው፡፡ በዕለተ ሐሙስ የተፈጠሩት ሦስቱ ፍጥረታት ዘመደ እንስሳ የሚባሉት ዓሣዎች ዘመደ አራዊት የሚባሉት አዞ፣ ጉማሬ፣ እንቁራሪት፣ ዘመደ አዕዋፍ የሚባሉት ዳክዬዎች ዝዬዎች ናቸው፡፡
በዕለተ ዓርብ እግዚአብሔር የፈጠራቸው ፍጥረታት በልብ የሚሳቡ በእግር የሚራመዱ በክንፍ የሚበሩ ናቸው፡፡ ሁሉንም የፈጠራቸው ሴትና ወንድ አድርጎ ነው፡፡ለምሳሌ የቤት እንስሳት ላም፣ በሬ፣ ፈረስ፣ በቅሎ፣ ፍየል፣ በግ ውሻ እና ድመት ናቸው፡፡
አዕዋፍ ዶሮ፣ ድንቢጥ፣ እርግብ ሌሎችም ናቸው፡፡ እንስሳት ለምሳሌ አጋዘን፣ ፊቆ፣ ሚዳቋ፣ ጎሽ፣ ዝሆን፣ ዋልያ የመሳሰሉት ናቸው፡፡
ቀዳሚት ሰንበት ማለት ቅዳሜ ማለት ነው፡፡ በዚች ዕለት ልዑል እግዚአብሔር ሊፈጥረው የወደደውን ሃያ ሁለቱን ሥነ ፍጥረት ፈጥሮ አከናውኖ አረፈባት፡፡ /ዘፍ.2፡2/ በመሆኑም እግዚአብሔር ባርኮ  የቀደሳትን ዕለት ማክበር ይገባል፡፡
ልጆች እስኪ ጥያቄ እንጠይቃችሁ
1ኛ. ሀልዮና ነቢብ ማለት ምን ማለት ነው?
2ኛ. ሔዋን እንዴት ተፈጠረች?
ልጆች በመጠኑም ቢሆን ሥነ ፍጥረትን እንዳወቃችሁ ተስፋ እናደር 
ጋለን፡፡ በተረፈ ሰንበት ትምህርት ቤት ሔዳችሁ ተማሩ እሺ ጎበዞች፡፡
Aba Giyorgise.JPG

የወርቃማው ዘመን ወርቃማ ደራሲ ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ

 Aba Giyorgise.JPG

መጋቢት 12 ቀን ከሰዓት በኋላ 6 ኪሎ በሚገኘው የኢትዮጵያ ስብሰባ ማዕከል፡፡

Aba Giyorgise M.JPG

ሀብዎሙ ዘይቤልዑ

የሚበሉትን ስጡአቸው(ክፍል አንድ)

በመ/ር አፈወርቅ ወ/አረጋዊ
ማቴ. 14.16

ከዓለም አስቀደሞ የነበረ በማእከለ ዘመን ያለ ዓለምን አሳልፎ ለዘለዓለም የሚኖር፣ ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል እግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ የተናገረው ቃል ነው፡፡ የሰውን ልጅ ለማዳን ከወደቀበት ለማንሣት ወደቀደመ ክብሩም ለመመለስ ከንጽሕተ ንጹሐን ከቅድስተ ቅዱሳን እመቤታችን ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ አምላክ ሰው ሆነ፡፡
በመዋዕለ ትምህርቱም የእጁን ተአምራት አይተው የቃሉን ትምህርት ሰምተው ከአሥር አህጉር ከብዙ መንደር ተውጣጥተው የአምስት ገበያ ያህል ሰዎች ይከተሉት ነበር፡፡
ከተከታዮቹም ውስጥ አሥራ ሁለቱ ሐዋርያት፣ ሰባ ሁለቱ አርድእት፣ ሠላሳ ስድስቱ ቅዱሳት አንስት በጥቅሉ መቶ ሃያ ቤተሰብ በመ ሆን /የሐዋ.1.15/፤ በዋለበት እየዋሉ በአደረበት እያደሩ ትምህርት ከተአምራት ሳይከፈልባቸው ሥጋዊ ፍላጎታቸውን አሸንፈው ተከትለውታል፡፡
«እኛ ሁሉን ትተን ተከተልንህ እንኪያስ ምን እናገኝ ይሆን» /ማቴ 19.27/፤ በማለት የአገልግሎት ዋጋ ከጠየቁት ሐዋርያት በተጨማሪም ሌላ  ብዙ ሕዝብ ይከተለው እንደነበር ወንጌላዊው ማቴዎስ እንዲህ በማለት ጽፎልናል «ከገሊላም ከአሥር ከተማም ከኢየሩሳሌምም ከአይሁድም ከዮርዳኖስም ማዶ ብዙ ሕዝብ ተከተሉት» /ማቴ. 4.25/፡፡
በዘመነ ብሉይ በነቢያት አድሮ ለሕዝቡ መልእክቱን ያስተላለፈ አምላክ ከነቢያት አንዱ በሆነው ልበ አምላክ ዳዊት ላይ አድሮ እንዲህ የሚል ቃል አናግሮ ነበር፡፡ «ወደ እርሱ ቅረቡ ያበራላችሁማል ፊታችሁም አያፍርም ይህ ችግረኛ ጮኸ እግዚብሔርም ሰማው ከመከራውም አዳነው» /መዝ. 33.5/፡፡
በምድራችን ላይ ብዙ ዓይነት ችግሮች ቢኖሩም ከረሀብ የበለጠ ችግር የለምና የራበው ሁሉ የሚበላውንና የሚጠጣውን ለማግኘት ወደ አምላኩ ይጮሃል፡፡ በሊቀ ነቢያት ሙሴ መሪነት ከግብፅ ባርነት ወደምድረ ርስት ሲጓዙ የነበሩ እስራኤላውያን በኃይለኛ ረሀብ ተመትተው ስለነበረ የምንበላውን ስጠን ብለው ወደ ሙሴ ጮኹ ይላል /ዘኁ. 21.4ጠ5/፡፡
ለቸርነቱ ወሰን ድንበር የሌለው፣ መግቦቱ የማይቋረጥ እግዚአብሔር ለተራቡት ሕዝብ መና ከደመና አዘነበላቸው፣ ውኃ ከዐለት ላይ አፈለቀላቸው፣ እነርሱም በሉ ጠገቡ ጠጡ ረኩ ይላል /ዘጸ. 16.8/፡፡
የፍጥረታት ሁሉ መጋቢ እግዚአብሔር አምላክ መሆኑን የተረዳው መዝሙረኛው፤ «የሁሉ ዓይን አንተን ተስፋ ያደርጋል አንተም ምግባቸውን በየጊዜው ትሰጣቸዋለህ አንተ እጅህን ትከፍታለህ ሕይወት ላለው ሁሉ መልካምን /የሚጠቅመውን/ ታጠግባለህ» ይላል /መዝ.144.15/፡፡
ስለ እርሱ የተነገረው ትንቢተ ነቢያት ተፈጽሞ ሰው ሆኖ በመጣ ጊዜም በነቢያት ያስተላለፈውን ጥሪ አማናዊ በማድረግ፤ «እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ ወደኔ ኑ … ለነፍሳሁም ዕረፍት ታገኛላችሁ ቀንበሬ ልዝብ ሸክሜ ቀሊል ነው» /ማቴ.11.28ጠ30/፤ በማለት የርኅራኄ ድምፁን አስምቷል፡፡
በዚህ ጥሪ መሠረት ልዩ ልዩ ችግር ያለባቸውን ማለትም በረሀብ የተጎዱትን ኅብስት አበርክቶ መግቧቸዋል፡፡ አካላቸው በበሽታ የደከመውን ፈውሶአቸዋል፡፡
ጌታችን የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ አንገት መቆረጡንና በድኑን ወስደው መቅበራቸውን ከደቀ መዛሙርቱ በሰማ ጊዜ ብቻውን ወደምድረ በዳ ፈቀቅ አለ፡፡ «ሕዝቡም ሰምተው ከከተማዎቹ በእግር ተከተሉት እርሱም ወጥቶ የተከተሉትን ሕዝብ አየና አዘነላቸው ድውዮቻቸውንም ፈወሰ፡፡» በልዩ ልዩ ችግር ተጠምደው መከራ በርትቶባቸው፣ ደዌ ሥጋ ደዌ ነፍስ አሠቃይቶአቸው የመጡትን በሽተኞች ከደዌ ሥጋ ከደዌ ነፍስ ፈወሳቸው፡፡ የሥጋ ረሀብተኞችንም ምግበ ሥጋን ሰጣቸው፤ በረሀበ ነፍስ የተጎዱትንም በቃሉ ትምህርት ፈወሳቸው፡፡ የእያንዳንዱን የችግር ቋጠሮ ሁሉ በአምላካዊ ጥበቡና ቸርነቱ ፈታላቸው እርሱ ሁሉን አዋቂ ነውና፡፡
ዛሬም እኛ ወደ እርሱ ከቀረብን ጉድለታችን ይሞላልናል፣ ያለው ይበረክትልናል፣ የራቀው ይቀርብልናል፣ አሳባችንን ችግራችንን በፍጹም እምነት በእርሱ ላይ እንተወው፤ /መዝ. 54.22/፡፡ የእኛ ድርሻ እርሱን መከተል ለእርሱ መታዘዝ ይሁን፤ በራት ላይ ዳረጎት እንዲሉ ሁሉ ይጨመርልናል /ማቴ. 6.33፡፡
ሁሉን ትተው የተከተሉት ደቀ መዛሙርቱ የእርሱ አገልጋዮችና የቅርብ ባለሟሎች ናቸውና፤ ለመምህራቸው ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀረብ ብለው በምስጢር፤ ቦታው ምድረ በዳ ነው አሁን ሰዓቱ መሽቷል ጊዜው አልፏል ወደመንደሮች ሔደው ለራሳቸው ምግብ እንዲገዙ ሕዝቡን አሰናብት፤ አሉት፡፡ እርሱ ግን ልብ ያሰበውን ኩላሊት ያመላለሰውን የሚመረምር ከአሳብ አስቀድሞ የሚታሰበውን የሚያውቅ አምላክ፤ በረሀብ የጠወለገ የደከመ ሰውነታቸው በበሽታ የተጎዳ አካላቸው በምግበ ሥጋ መጠንከር ነበረበትና፡፡ ደቀ መዛሙርቱን «የሚበሉትን ስጡአቸው እንጂ በረሀብ በተጎዳ ሰውነታቸው ሊሄዱ አያስፈልግም አላቸው፡፡»
በሥጋ አለስልሶ በደም አርሶ በጅማት አስሮ በአጥንት አጠንክሮ የፈጠረውን ሰውነት ለደቂቃ እንኳን ሳይዘነጋ በዝናብ አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ የሚመግብ አባት ነው፡፡
ለዘሪ ዘርን ለመብላትም እንጀራን በብዙ የሚሰጥ እርሱ የምድርን ፍሬ አንዲቷን ቅንጣት በመቶ፣ በሺሕ አብዝቶ የፈጠረውን ፍጥረት ዓለም ከተፈጠረ ዘመን ከተቆጠረ ጀምሮ ሳያቋርጥ ከትንኝ እስከ ዝሆን ከሰው እስከ እንስሳ ያለውን እርሱ ባወቀ መመገብ የሚገባውን ሁሉ የሚመግብ አምላክ ነው፡፡
ስለሆነም የእርሱን ርኅራኄ የሐዋርያትን መብትና ግዴታ ለመግለጥ፤ የሚበሉትን ስጡአቸው አለ፡፡ እነርሱም የአምላካቸውን የመምህራቸውን ትእዛዝ በፍጹም ፍቅር በመቀበል መስጠትስ ይቻል ነበር ነገር ግን ያለው ጥቂት ነው፡፡ ከአምስት እንጀራና ከሁለት ዓሣ በቀር የለም ለዚህ ሁሉ ሕዝብ አይበቃም ነው ያሉት፡፡
አስደናቂው ነገር ደቀ መዛሙርቱ የምግቡን ማነስ ተናገሩ እንጂ ይህ አምስት እንጀራና ሁለት ዓሣ እንኳን ለሌላው ለእኛም አይበቃም፡፡ እኛ ምን እንበላለን የሚል የስስት የስግብግብነት አስተሳሰብም ሆነ ንግግር አላደረባቸውም፡፡ ከሕዝቡ ብዛት የተነሣ ግን በሰው ሰውኛው አመለካከት አለመብቃቱን ገልጸዋል፡፡
ዓለም እጅግ ብዙ ነገር ይፈልጋል ብዙ ነገር ይሰበስባል ያከማቻል ነገር ግን ያንሰዋል፡፡ የሰበሰበው ይበተናል የሞላው ይጎልበታል፤ ይገርማል በእግዚአብሔር ዘንድ የተሰጠ ከሆነ ግን ጥቂቱ ይበቃል፤ /ሉቃ. 10.42/፡፡
እርሱም የያዛችሁትን ያለውን አምጡልኝ አላቸው፡፡ አመጡለት በእርሱም እጅ ላይ አበረከተው፡፡ እኛም እንደ ደቀ መዛሙርቱ ያለንን ይዘን ወደ እርሱ እንቅረብ ከእርሱ መደበቅ የለብንም፤ አሥራቱን በኩራቱን ቀዳምያቱን ስሙ ለሚጠራበት ቤተ ክርስቲያን እንስጥ፤ ወደ እርሱ ይዞ መቅረብ ማለት ይህ ነውና ለእኛ በቅቶ ለሌላው ይተርፋል፡፡
ያለምንም ቅሬታ ማጉረምረም ትእዛዙን ተቀብለው የያዙትን ወደ አምላካቸው አቀረቡት፡፡ ምእመናን ቅር ሳይላቸው ሳያጉረመርሙ እንደ ደቀመዛሙርቱ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ መቀበል አለባቸው፡፡ ጌታችንም የቀረበውን እንጀራ ባረከው፡፡ ከባረከው በኋላ ቆረሰው ለደቀ መዛሙርቱ ሰጣቸው ሥራው ሁሉ ድንቅ ነውና የሰጣቸው ሁሉ በእጃቸው ላይ ይበረከት ነበር፡፡ «እግዚአብሔርን ሥራህ ግሩም ነው በሉት» /መዝ. 25.3/፡፡
ለጌታ የሰጡትን ከጌታም የተቀበሉትን እንጀራ በአካባቢው ለነበረው ሕዝብ ሁሉ ሰጡ አቀረቡ፤ ሕዝቡን አስተናገዱ፡፡ እነርሱም የመመገብ የማስተናገድ ሓላፊነት አገኙ፤ ሁሉም በልተው ጠገቡ፤ ከነበሩት ሁሉ ያልበላ አልተገኘም፡፡ መብላት ብቻ ሳይሆን እስከሚበቃቸው ድረስ በሉ አተረፉ፡፡ እውነት ነው ከአምላክ የተሰጠ ሁሉ ያጠግባል፡፡ ይትረፈረፋል፡፡
ቀድሞ በሊቀ ነቢያት ሙሴና በሊቀ ካህናት አሮን ላይ አድሮ፤ መና ከደመና አውርዶ፣ ውኃ ከዐለት አፍልቆ፣ አእላፈ እስራኤልን የመገበ ያጠጣ፣ ከሁሉ በላይ የሆነ፣ በሁሉ ያለ በሁሉ የሚሠራ ኃያል አምላክ፤ በብሉይ ኪዳን ሰው ሊደርስበት በማይችል ረቂቅ ጥበቡ ይሠራው የነበረውን መግቦት ሰው በመሆን በሚታይ በሚዳሰስ በሚጨበጥ ሰውነት /አካል/ እጁን ወደሰማይ በመዘርጋት፤ ሥርዓተ ጸሎትን አድርሶ፣ ሥርዓተ ምግብን አስተምሮ፣ እንጀራውን ፈትቶ /ቆርሶ/ እንካችሁ ብሎ በመስጠት ሰዎችን መገበ፡፡ እርሱ ከመገበ የማይመገብ ማን አለ) እሱ ከሰጠ የማይቀበልስ ማን አለ) ሁሉም ከተመገቡ በኋላ የተረፈው ማዕድ ሲነሣ አሥራ ሁለት መሶብ ሙሉ ሆነ በእሱ ሥራ ጉድለት የለምና ከሴቶች ከልጆች በቀር አምስት ሺሕ ወንዶች ያህሉ ነበር፡፡
ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት የተናገረው ቃል ምንኛ ያማረና የተወደደ እውነተኛ ቃል ነው፡፡ «በሉ እጅግ ጠገቡ ለምኞታቸውም ሰጣቸው ከወደዱትም አላሳጣቸውም» /መዝ.77.29/ እንዲል፡፡
እውነት ነው አምላካችን ሲመግበን እንጠግባለን፤ መልካም ምኞታችን የተሳካ ሥራችን የተከናወነ፣ ምርታችን የተትረፈረፈ፣ አገልግሎታችን የተቀደሰ፣ ዕውቀታችን የመጠቀ፣ አስተሳሰባችን የረቀቀ ከመሆን ባሻገር ከእኛ አልፎ ተርፎ ለሌላው የሚሆን የበረከት እንጀራ ይገኛል፡፡ይህ ሊሆን የሚችለው ደግሞ በሥርዓቱ ስንመራና በተሰጠን የሕይወት መንገድ ወደቀኝ ወደ ግራ ሳንል መራመድ ስንችል ነው /ኢያ. 1.7/፡፡
ይቆየን፡፡

ገብርሔር

በዲ/ን አባተ አስፋ
ዛሬ ታላቁን የጌታችንን ጾም ከጀመርን ስድስተኛ ሳምንት ላይ ደርሰናል፡፡ ይህን ሳምንት ቅድስት ቤተክርስቲያን «ገብርሔር» የሚል ስያሜ ሰጥታዋለች፡፡ ገብርሔር በጎ አገልጋይ ማለት ሲሆን የስያሜውን መነሻ የምናገኘው በዕለቱ ሥርዓተ ቅዳሴ ከሚነበበው የወንጌል ክፍል ማቴ.25-14-30 ነው፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምሳሌ መስሎ ካስተማራቸው ትምህርቶች መሀከል አንዱ የሆነው ይህ የዛሬው ወንጌል አስተማሪ የሆኑ መሠረታዊ ጉዳዮችን በውስጡ ይዟል፡፡ በተለይ ምንም እንኳን የቤተክርስቲያን ሓላፊነት የእገሌና የእገሊት ተበሎ ባይወሰንም ቅሉ ቤተክርስቲያን ባላት የአገልግሎት መዋቅር መሠረት የሓላፊነትን ቦታ ይዘው ለሚያገለግሉ ሰዎች አትኩሮት ሊሰጡባቸው የሚገባቸውን ነጥቦች ይጠቁማል፡፡ ይህን ለማየት ያመቸን ዘንድ ከታሪኩ የመጀመያ ክፍል በመነሣት ዋና ዋና የሆኑ አሳቦችን በአትኩሮት መመርመር ጠቃሚ ነው፡፡

በምሳሌያዊው ታሪክ መጀመሪያ ላይ የምናገኘው አንድ መንገድ ሊጀምር ያሰበ ሰው ከመሔዱ በፊት አገልጋዮቹን ጠርቶ ለእያንዳንዳቸው እንደ ችሎታቸው መጠን ለአንዱ አምስት ለአንዱ ሁለት እንዲሁም ለሌላኛው አንድ መክሊት ነግደው ያተርፉበት ዘንድ እንደሰጣቸው ነው፡፡

ገና ከታሪኩ መጀመሪያ እንደምንረዳው የአገልጋዮቹ ጌታ ምንም እንኳን እርሱ ለመንገድ ቢዘጋጅም ሀብቱ ግን በተዘጋ ቤት ውስጥ ተቆልፎበት እንዲቀመጥ አልፈለገም፡፡ በዚህም አገልጋዮቹን ጠርቶ ገንዘቡን በአደራ ተቀብለው «እንዲያተርፉበት» ማዘዙን እንደማስረጃ ልናቀርብ እንችላለን፡፡ ሆኖም ግን ማትረፍ በመፈለጉ ብቻ ገንዘቡን ያለአግባብ አልበተነም፡፡ ነገር ግን ለእርሱ ቀረቤታ የነበራቸውን አገልጋዮቹን ጠርቶ ያውም እንደየችሎታቸው መጠን ሓላፊነቱ ሳይከብዳቸው እንዲሠሩበት ገንዘቡን አከፋፈላቸው፡፡

ይህ ጌታ ቅንነትና ርኅራኄ የበዛለት እንደሆነ የሚያመላክተን ነገር አለ፡፡ ይኸውም ለአገልጋዮቹ ሓላፊነትን ቢሰጥም እንኳን ከእነርሱ ጋር በነበረው ቀረቤታ ማን ምን መሥራት ይችላል የሚለውን ከግምት ውስጥ በማስገባት ለእያንዳንዳቸው እንደ ሓላፊነት የመሸከም አቅማቸው አምስት ሁለት አንድ እያደረገ መስጠቱ ነው፡፡

ምናልባት ስስት ባልተላቀቀው ስሜት ለሚያስብ ሰው የዚህ ጌታ መክሊት አሰጣጥ አድልዎ ያለበት ሊመስለው ይችላል፡፡ ታሪኩን እስከ መጨረሻው ብንከታተለው ግን የሚያሳየን የባለ መክሊቱን ባለቤት ቅንነት ነው፡፡ ቀጥለን እንደምናነበው ይህ ጌታ ለአገልጋዮቹ አትርፉበት ብሎ መክሊቱን ሰጥቷቸው በሔደበት ሀገር አልቀረም፡፡ ይልቁንም እያንዳንዱ በተሰጣቸው መክሊት ምን እንደሠሩበት ሊቆጣጠራቸው እንደመጣ እናነባለን፡፡ ስለዚህ አገልጋዮቹ በሰጣቸው መክሊት ምን እንደሠሩ እንደሚጠይቃቸው እያወቀ ከአቅማቸው በላይ የሆነ መክሊትን በመስጠት ምን ሠርተው የተሰጣቸውን መክሊት ያህል ማትረፍ እንደሚችሉ በማሰብ እንዲጨነቁ አልፈለገም፡፡ በተቃራኒው የምናየው ያለምንም ጭንቀት ከአእምሯቸው በላይ ሳይሆን ባላቸው ኃይል ተጠቅመው መሥራትና ማትረፍ የሚችሉትን ያህል መክሊት እንደሰጣቸው ነው፡፡

ከብዙ ጊዜም በኋላ የእነዚያ አገልጋዮች ጌታ በሰጣቸው መክሊት ምን እንደሠሩበት ሊቆጣጠራቸው ሲመጣ አምስት መክሊት ተቀብሎ የነበረው ሌላ አምስት እንዲሁም ሁለት መክሊት ተቀብሎ የነበረው ሌላ ሁለት መክሊት አትርፎ ጌታቸው ፊት እንደቆሙ ያ ጌታም በእነዚህ አገልጋዮቹ ታማኝነት ተደስቶ ወደ ደስታው እንዳስገባቸው እናያለን፡፡ በተቃራኒው ደግሞ ያ አንድ መክሊት ተቀብሎ የነበረው ምድርን ቆፍሮ ያተርፍባት ዘንድ የተሰጠችውን መክሊት እንደቀበረ ከዚህም አልፎ ምን አደረክባት ተብሎ ሲጠየቅ የአመጽ ንግግር እንደተናገረ በዚህ ከፊቱ ያዘነው ጌታውም ያን ክፉ አገልጋይ እንዲቀጣ እንዳደረገው አናነባለን፡፡

በዚህኛው ክፍል ከተጠቀሰው ታሪክ ሦስቱን አካላት ማለት የመክሊቱን ሰጪ ጌታ፣ በጎ የተባሉ አገልጋዮችና ክፉ እና ሰነፍ የተባለውን አገልጋይ በተናጥል እንመልከታቸው፡፡

1. የአገልጋዮቹ ጌታ፡-

ይህ ሰው ለገንዘቡ ጠንቃቃ ከመሆኑ ባሻገር በአገልጋዮቹ ላይ ሙሉ ሥልጣን እንዳለው እናያለን፡፡ በክፉው አገልጋይ ላይ ባለመታዘዙ ምክንያት የፈረደበትን ፍርድ /ልቅሶና ጥርስ ማፏጨት ወዳለበት በውጪ ወዳለ ጨለማ አውጡት/ ስንመለከት የሚያሳየን የአገልጋዮቹን ጌታ ታላቅ ሥልጣን ነው፡፡ ምንም እንኳን ሥልጣኑ ጽኑ ቢሆንም ይህ ጌታ ፍርዱ ግን በእውነት ላይ የተመረኮዘ መሆኑን ደግሞ በድካማቸው ታግዘው በተሰጣቸው መክሊት ላተረፉት በጎ አገልጋዮች የሰጣቸውን ፍጹም ደስታ መጥቀስ ይቻላል፡፡

2. በጎ አገልጋዮች:-

በአገልጋዮቹ ጌታ በጎ አገልጋዮች የተባሉት አምስት መክሊት የተቀበለውና ሁለት መክሊት የተቀበለው ናቸው፡፡ እዚህ ጋር ማስተዋል የሚገባው እነዚህ ሁለቱ አገልጋዮች በጎ አገልጋዮች ለመባል ያበቃቸው አስቀድመው ብዙ ወይንም የተሻለ ቁጥር ያለው መክሊት ለመቀበል መብቃታቸው አይደለም፡፡ ጉዳዩ የመክሊቱ ቁጥር ሳይሆን በተሰጣቸው መክሊት መጠን የሚገባቸውን ያህል ደክመው ማትረፍ መቻላቸው ነው፡፡ ወይንም ያ ባለ አንድ መክሊት አገልጋይ ከሁለቱ ያሳነሰው ከአንድ በላይ መክሊት መቀበል የማይችል መሆኑ ሳይሆን በዚያችው በአንዷ መክሊት እንኳን መሥራት አለመቻሉ ነው፡፡

3. ክፉና ሰነፍ አገልጋይ:-

ይህ ሰው የተጠቀሱ ሦስት መሠረታዊ ችግሮች አሉበት፡፡

ሀ. የአገልጋዮቹ ጌታ ወደ መንገድ ሊሔድ በተዘጋጀበት ወቅት አገልጋዮቹን ጠርቶ ለእያንዳንዳቸው እንደችሎታቸው ገንዘቡን ሲሰጣቸው አትርፈው እንዲቆዩት ነው፡፡ ከላይ እንደተነገጋገርነው እንደ አቅማቸው መስጠቱም አቅማቸው በሚፈቅደው የሥራ ደረጃ እንዲሰማሩ በማሰብ ነበር፡፡ ይህ ሰነፍ አገልጋይ ግን ያደረገው ከታዘዘበት ዓላማ በተቃራኒው መልኩ ነው፡፡ ሊሠራበት የሚገባውን መክሊት ቀበረው፡፡ ይህም ለጌታው ትዕዛዝ ያለውን ቸልተኝነት ያሳያል፡፡

ለ. ጌታው በመጣ ጊዜ አመጽ የተመላበት የሐሰት ንግግር ተናግሯል፡- ከሔደበት ቦታ ተመልሶ ጌታው በተሰጠው መክሊት ምን እንዳደረገ ሲጠይቀው «አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፣ ካልበተንህበትም የምትሰበሰብ ጨካኝ ሰው እንደ ሆንህ አውቃለሁ ስለፈራሁም ሔድሁና መክሊትህን በምድር ውስጥ ቀበርሁ፡፡» ሲል መለሰለት፡፡ ይህ ንግግር ከአመጽ ንግግርነቱ በተጨማሪ ውሸት አለበት፡፡ ምክንያቱም እርሱ እንዳለው ጌታው ካልዘራበት የሚያጭድ ካልበተነበት የሚሰበሰብ ጨካኝ ሰው ቢሆን ኖሮ ያደርግ የነበረው ምንም መክሊት ሳይሰጠው ከነትርፉ ሁለት መክሊቶችን ይጠይቀው ነበር፡፡ ነገር ግን ተጽፎ የምናነበው ትርፉን ከመጠየቅ በፊት አንድ መክሊት ሰጥቶት እንደበረ ነው፡፡ ይህ ማለት ደግሞ አስቀድሞ ገንዘቡን ዘርቶ ነበር ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ይህ ጌታ ዘርቷልና ማጨድ ይገባዋል፤ በትኗልና መሰብሰብም መብቱ ነው፡፡

ሐ. እርሱ መሥራት ሲሳነው እንኳን ዕድሉን ለሌሎች አልሰጠም፡- ይህ ሰው የተሰጠው መክሊት በትርፍ ሊመለስ እንደሚገባው ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ ምክንያቱም ገና ሲቀበል ከጌታው የተቀበለው ትዕዛዝ ነውና፡፡ ስለዚህ ምንም እንኳን መውጣት መውረዱ ቢከብደውም ወጥተው ወርደው ማትረፍ ለሚችሉ ሰዎች አለመስጠቱ ተጨማሪ ጥፋቱ ነው፡፡ ይህን እንዳያደርግ ያሰረው ደግሞ ውስጡ የተቀረጸው የአመጽ መንፈስ ነው፡፡ ጌታው መጥቶ ስለ ትርፉ ሲጠይቀው የሚመልስለትን ረብ የለሽ ምክንያት እንደ መከላከያ አድርጎ ማሰቡ አእምሮው ሌላ አማራጭ እንዳያስብ የዘጋበት ይመስላል፡፡

የመጽሐፈ ቅዱስ መተርጉማን አባቶች የዚህን ምሳሌያዊ ታሪክ ምስጢር ሲያስተምሩ የአገልጋዮቹ ጌታ የፍጡራን ጌታ የሆነ የእግዚአብሔር ምሳሌ እንደሆነ እንዲሁም ሦስቱ አገልጋዮች በተለያየ ደረጃ ያሉ ምዕመናንን እንደሚወክሉ ያስተምራሉ፡፡

ከዚህ የወንጌል ክፍል ምን እንማራለን?

ከተጠቀሰው ታሪክ የምንማራቸው ብዙ ነገሮች ቢኖሩም አበይት የሆኑትን ሁለቱን እንመልከታቸው፡፡

1. ለእያንዳንዳችን ከእግዚአብሔር የተሰጠ ስጦታ እንዳለ እንረዳበታለን

እግዚአብሔር እያንዳንዳችን በሃይማኖት ሆነን የምናፈራውን ፍሬ ይፈልጋል፡፡ ምንም እንኳን ከእኛ ፍሬን ቢፈልግም ያን ፍሬ ማፍራት የምንችልበትን ኃይል ግን የእግዚአብሔርን ልጅነት ካገኘንበት ከዕለተ ጥምቀት ጀምሮ እንደሚያስፈልገን መጠን እየሰጠን ነው፡፡

ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቀበልናቸው ስጦታዎች በቁጥር እጅግ ብዙ ቢሆኑም በአይነታቸው ግን ለሁለት ከፍሎ ማየት ይቻላል፡፡ የመጀመሪያው እያንዳንዱ ክርስቲያን ዳግመኛ በመወለድ ምስጢር ያገኘው የእግዚአብሔር ልጅነት ጸጋና ከልጅነት ጋር በተያያዘ የሚሰጡ ስጦታዎች ናቸው ፡፡ዮሐ.3-3 ሁለተኛው አይነት ደግሞ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድና እንደ ሰውየው አቅም ለተለያዩ መንፈሳዊ አገልግሎቶች ማስፈፀሚያ ይሆኑ ዘንድ በእግዚአብሔር የሚሰጡ ስጦታዎች ናቸው፡፡ ለምሳሌ ትንቢት መናገር ፣ በተለያዩ ልሳናት መናገር ፣ አጋንንትን ማስወጣት … የመሳሰሉት ከዚህኛው አይነት ስጦታ የሚመደቡ ናቸው፡፡ 1ኛ ቆሮ.12-4፡፡

በመጀመሪያውም ይሁን በሁለተኛው አይነት ስጦታ ተቀባዮች ዘንድ ግን ብዙ የሚያሳዝኑ ችግሮች አሉ፡፡ በዳግመኛ መወለድ ምሥጢር (በ40 ና 80 ቀን ጥምቀት) ስላገኘነው የልጅነት ጸጋ ጊዜ ሰጥቶ የሚያስብ ክርስቲያን ማግኘት በዚህ ዘመን በጣም አዳጋች ነው፡፡ በዓመት ውስጥ ክርስቲያንነቱ ለጥምቀት በዓልና ለመስቀል ደመራ ካልሆነ ትዝ የማይለው ቁጥሩ ቀላል አይደለም፡፡ ከዚህ የከፋው ደግሞ ከቤተ ዘመድ አንድ ሰው ምናልባትም ራሱም ሊሆን ይችላል ነፍሱ ከሥጋው ካልተለየች ወደ ቤተ ክርስቲያን ደጅ ብቅ አይልም፡፡

እግዚአብሔር ለእኛ የልጅነትን ጸጋ በመስጠቱ ለእኛ ያለውን ጥልቅ ፍቅሩን አሳይቶናል፡፡ ምክንያቱም ልጅነታችን ዋጋ ተከፍሎበታልና፡፡ እንዲሁ በቀላሉ አይደለም ልጆች የተባልነው፡፡ እኛ ልጅነትን እንድንቀበል አምላክ መከራን ተቀብሏል፡፡ የጥምቀታችን ውሃ የፈሰሰው በጦር ከተወጋው ከጌታ ጎን ነው ፡፡ ዮሐ.19-24፡፡

ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ይሄንን ሁሉ ሲያመለክት ‹‹የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን ልንጠራ አብ እንዴት ያለውን ፍቅር እንደሰጠን እዩ፡፡›› 1ኛ ዮሐ.3-1 ያለው፡፡

እኛ ልጆቹ እንሆን ዘንድ እግዚአብሔር ካሳየን የአባትነት ፍቅር በተጨማሪ ልጆቹ ስለመሆናችን የገባልንም ተስፋ ከአዕምሮ በላይ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለገላትያ ምዕመናን በላከው መልእክቱ ‹‹እንኪያስ እናንተ ልጆች ናችሁ እንጂ ባሮች አይደላችሁም፡፡ ልጆች ከሆናችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሾች ናችሁ፡፡›› ገላ.4-7 ስለሚጠብቀን ተስፋ ነግሮናል፡፡

ትልቁ ችግር ግን ተጠማቂው ሰው ይህን የልጅነት ክብር አለመረዳቱ ነው፡፡ የልጅነቴን ክብር ተረድቻለሁ እያለ የሚያወራውም ቢሆን የልጅነቱን መክሊት በልቡናው ውስጥ ቀብሮ አንድም ፍሬ ሳያፈራ ስለማንነቱ ለማውራት ቃላት ሲመርጥ ጊዜውን ያባክናል፡፡ አብዛኛው ግን የክርስትና እምነት ደጋፊ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ልጅነት ሊገለጥ የሚገባው እንደ ሀገር ልጅነታችን በምናሳየው የደጋፊነት /የቲፎዞነት/ ስሜት አይደለም፡፡ ደጋፊነት በጊዜ ና በቦታ ለተወሰነ ያውም ኃላፊ ለሆነ ድርጊት ነው፡፡ ክርስትና ግን በማንኛውም ቦታ፣ ጊዜ የሚኖርበት የህይወት መስመር እንጂ የሚደገፍ ጊዜያዊ ድርጊት አይደለም፡፡

ስለዚህ በጣም ልንጠነቀቅበት የሚገባን የመጀመሪያው መክሊታችን ልጅነታችን መሆኑን መረዳት ያስፈልገናል፡፡በዚህም መክሊት እንድንሰራ የታዘዝናቸውን ምግባራት እንድናፈራ የሚጠበቅብንን ፍሬዎች ማፍራት አለብን፡፡ ያለበለዚያ መክሊቱን እንደቀበረው ሰው መሆናችን ነው፡፡

2. እያንዳንዱ ስጦታ እንደሚያስጠይቅ እንረዳለን

እግዚአብሔር ያለ አንድ አላማ ለሰዎች ኃላፊነትን የሚያሰከትል ስጦታ አልሰጠም አይሰጥምም፡፡ ማንም ከእግዚአብሔር የተቀበለ ሰው የተሰጠው ስጦታ ለሆነ አላማ ነውና ጥያቄ አለበት፡፡ ጠያቂው ደግሞ የስጦታው ባለቤት ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡

መንጋውን እንዲጠብቁለት ሥልጣንና የተለያዩ የአገልግሎት ሰጦታዎችን እግዚአብሔር የሰጣቸው አሉ፡፡ዮሐ. 21-15 ፤ ገላ.1-15-16፡፡ ሆኖም ግን የተሰጣቸው ኃላፊነት የሚያስጨንቃቸው፣ ከልባቸው በእውነተኛ ትህትና የሚተጉ ያሉትን ያህል የሚያገለግሉበትን ስጦታ ከእግዚአብሔር መቀበላቸውን እንዲሁም የሚያስጠይቃቸው መሆኑን እስኪዘነጉ ድረስ መንገዳቸውን የሳቱ አሉ፡፡ በእግዚአብሔርና በሰዎች መሀከል እንደ ድልድይ ሆነው ያገለግሉበት ዘንድ በተሰጣቸው ሥልጣን እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ተግባር የሚፈፅሙ ሰዎች ለዚህ ጥሩ ምሳሌዎች ናቸው፡፡

እንዲሁም ደግሞ ተሰባኪውን ወደ እግዚአብሔር ከመምራት ይልቅ የነሱ ደጋፊ፣ ስለክብራቸው ተሟጋች እንዲሆን በህዝቡ መሀከል ጎራ እንዲፈጥርና የጳውሎስ ነኝ የአጵሎስ ነኝ እንዲል የሚያደርጉት ሰባኪዎችም ሌሎች ተጠቃሾች ናቸው፡፡ ማንም ይሁን ማን ግን ስለተሰጠው መክሊት ባለቤቱ ከፊቱ አቁሞ እንደሚጠይቀው መዘንጋት የለበትም፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

Aba Entones Gedam.JPG

በዓለማችን የመጀመሪያ የሆነው የአባ እንጦንስ ገዳም በዐሥራ አራት ሚሊዮን ዶላር እድሳት ተደረገለት

ገዳሙ አንድ ሺሕ ስድስት መቶ ዓመታትን አስቆጥሯል

በሻምበል ጥላሁን

በዓለም የመጀመሪያው የምንኩስናና የገዳማውያን ኑሮ መሥራች የሆነው የአባ እንጦንስ ገዳም በግብፅ መንግሥት በዐሥራ አራት ሚሊዮን ዶላር ወጪ እድሳት ተደርጎለት ለአገልግሎት መዘጋጀቱን ቢቢሲ የካቲት 4 ቀን 2002 ዓ.ም ዘገበ፡፡ በግብፅ የሚገኘው የቅዱስ እንጦንስ ገዳም ከአንድ ሺሕ ስድስት መቶ ዓመት በላይ ዕድሜ ያለው ጥንታዊ ገዳም ነው፡፡

Aba Entones Gedam.JPG 

በግብፅ የሚገኘው የአባ እንጦንስ ገዳም 

ገዳሙ ከዕድሜ ብዛት በእርጅና ከደረሰበት ጉዳት ተጠግኖ ለቱሪስት ኢንዱስትሪው ተጨማሪ አቅም እንዲፈጥር የግብፅ መንግሥት ከዐሥራ አራት ሚሊዮን ዶላር በላይ ወጪ እንዳደረገ ዘገባው ጠቁሞ፤ ገዳሙ መንፈሳዊ እሴቱና ታሪካዊ ዳራው እንዳይጠፋ ለማደስ ከስምንት ዓመት በላይ እንደፈጀም የዜና ምንጩ አስታውቋል፡፡

የቢቢሲ ዘገባ እንዳመለከተው፤ የገዳሙ መታደስ የሀገሪቱን የቱሪስት ኢንዱስትሪ ከማስፋፋቱም በላይ ከፍተኛ የኢኮኖሚ አቅም ለመገንባትም እንደሚያስችል አመልክቷል፡፡

በግብፅ ስዊዝ ከተማ የሚገኘው የአባ እንጦንስ ገዳም መታደስ፣ አገልግሎት ላይ መዋልና ለቱሪስት መስህብነት ክፍት መሆኑ፤ ሀገሪቱ የቀድሞ ታሪኳንና ቅርሷን ለመጠበቅ የምታደርገውን ጥረት እንደሚያሳይ ዛሒ ሐዋስ የተባሉት የግብፅ ዋና የቅሪተ አካል ተመራማሪ መናገራቸውንም የዜና ምንጩ አስታውቋል፡፡

ገዳሙ ቅዱስ እንጦንስ በሦስተኛው መቶ ከፍለ ዘመን በቀይ ባሕር አካባቢ በሚገኘው ተራራማና በረሐማ አካባቢ ለጸሎት የመነኑበት ቦታ ነው፡፡

በመልሶ ግንባታው ወቅት በገዳሙ የሚኙት ሁለት አብያተ ክርስቲያናትና ሁለት ማማዎች በጥንቃቄ መንፈሳዊና ታሪካዊ ይዘታቸው ሳይቀየር መሠራታቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡

የቅዱስ እንጦንስ ገዳም በግብፅ ኦርቶዶክሶችም ሆነ በአምስቱ ኦሪየንታል አኀት አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ ታዋቂ ነው፡፡

በገና እንደርድር

 በመ/ር መንግስተአብ አበጋዝ
ለግማሽ ምእተ ዓመት ያህል በገና ለደረደሩት መጋቤ ስብሐት ዓለሙ አጋ እሑድ የካቲት 14 ቀን 2002 ዓ.ም ልዩ ነበር፡፡ ስለዚህ በገናቸውን አንሥተው መጋቤ ስብሐት «ማን ይመራመር ማን ይመራመር ያንተን ሥራ ያንተን ግብር ማን ይመራመር …» እያሉ ያመሰግናሉ፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ለስድስት ወር ያሠለጠናቸው አርባ ስድስት የበገና ደርዳሪዎችን በሩሲያ ባሕል ማእከል የፑሽኪን አዳራሽ ተመልክተዋልና፡፡

«ለረዥም ዘመን ብቸኝነት ይሰማኝ  ነበር» ያሉት መጋቤ ስብሐት ዓለሙ፡፡ «አሁን በዝተናል» በማለት የበገና ማሠልጠኛዎችም ሆኑ ተማሪዎቹ እየጨመሩ መምጣታቸው ሀገራዊ እሴቱንም ሆነ ሃይማኖታዊ ሥርዓቱን ጠብቆ ለማየቆት ጠቃሚ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መመሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የተቋቋመው የአቡነ ጎርጎርዮስ ትምህርት ቤት በአብነት ትምህርትና በዜማ መሣሪያዎች እያሠለጠነ ማስመረቅ ከጀመረ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ እንደ ት/ቤቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ አዲስ ተፈራ ገለጻ የዛሬውን ጨምሮ አሥራ አራት ዙር አሠልጥኖ አስመርቋል፡፡

ሥራ አስኪያጁ የአብነት ትምህርትና የዜማ መሣሪያዎች ሥልጠና እሴቶቹን ከመጠበቅ ባሻገር የሚያስገኙትን መንፈሳዊና ማኅበራዊ ጠቀሜታዎች ሲዘረዝሩ «ለምስጋና፣ ለተመስጦ፣ ጭንቀትንና ርኩስ መንፈስን ለማራቅ፣ ለትምህርት፣ እንዲሁም የሀገርን ቅርስ ከነሙሉ ታሪኩና ጥቅሙ ለማስተዋወቅ፣ ትውፊትን ለትውልድ ለማውረስና በገና ከነበረው ጥቅም አንጻር ቀጣይ አገልግሎት እንዲኖረው ማድረግ ይቆይ የማይባል አገልግሎት ነው፡፡» ይላሉ፡፡

ወጣት ሚልካ ሐጎስ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የአምስት ኪሎ ኢንጂነሪንግ የ4ኛ ዓመት ተማሪ ናት፡፡ ከትምህርቷ በተጓዳኝ ትምህርተ ቤተ ክርስቲያን የምትከታተል የግቢ ጉባኤ ተማሪ ናት፡፡ በዚህ ሁሉ የጊዜ ጥበት ግን በአቡነ ጎርጎርዮስ ት/ቤት የሚሰጠውን የዜማ መሣሪያ ሥልጠና ወስዳ በበገና መደርደር ተመርቃለች፡፡ ሚልካ ጊዜዋን አጣጥማ በሳምንት ሁለት ቀን ለሁለት ሰዓት ተከታትላ በስድስት ወር ያጠናቀቀችውን ሥልጠና እንዴት ትገልጠዋለች)

«ጊዜአችንን በአግባቡ የምንጠቀም ከሆነ ሕልምን እውን ማድረግ እንችላለን፡፡ ጊዜዬን ተጠቅሜ በገና ተምሬአለው፡፡ ይህ ለእኔ መንፈሳዊ ሕይወት እጅግ አጋዤ ነው፡፡ ጊዜ መድቤ ደግሞ የአብነት ትምህርቱንና ተጨማሪ የዜማ መሣሪያዎችን ለመማር አስባለሁ፡፡ እድሜዬን ሁሉ አገልጋይ ሆንኩ ማለት አይደል፡፡ በእውነት በገና መደርደር መታደል ነው፡፡» ብላለች፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም ትምህርት ቤቱን ከፍቶ ኑና በገና እንደርድር ይላል፡፡

ከጋምቤላ ክልል የመጡ ሠልጣኞች ተመረቁ

በማኅበረ ቅዱሳን የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ክፍል አስተባባሪነት ከጋምቤላ ክልል የአኝዋክና የኑዌር ብሔረሰብ ተወላጅ ሠልጣኞች ተመረቁ፡፡ በማኅበረ ቅዱሳን የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ሓላፊ ዲ/ን አንዱአምላክ ይበልጣል እንደተናገሩት በክልሉ ከ1997 ዓ.ም ወዲህ ሠልጣኞች መጥተው ሲሠለጥኑ የአሁኑ የመጀመሪያ ጊዜ ነው፡፡

ሓላፊው የሥልጠናውን ዓላማ ሲያስረዱ በአብዛኛው የጠረፋማ ቦታዎች የሚገኙ ብሔር ብሔረሰቦች በቋንቋቸው የሚያስተምራቸው ባለማግኘታቸው ተቸግረው ቆይተዋል፡፡ ይህንን ለማቃለል ከማኅበረሰቡ የተገኙ ወጣቶችን በማስተማር ወደ ትውልድ ቀዬአቸው ተመልሰው ሕዝቡን እንዲያስተምሩና እንዲያስጠምቁ ለማድረግ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ላሬ፣ ኝንኛንግ፣ ፒኝዶ፣ አበቦ፣ ጆር፣ ኢታንግ እና ጋምቤላ ዙሪያ ከሚባሉ ሰባት ወረዳዎች የመጡት ሠልጣኞች በቁጥር ዐሥራ ስድስት ሲሆኑ ሥልጠናው ዐሥራ አምስት ቀን እንደወሰደ ሓላፊው ተናግረዋል፡፡

ሥልጠናውን ለመሥጠት ከሰላሳ አምስት ሺሕ ብር በላይ ወጪ እንዳስፈለገ የጠቀሱት ሓላፊው ወደፊትም በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚገኙ በጎ አድራጊዎች ይህንን መሰል መንፈሳዊ አገልግሎት ለማከናወን የእርዳታ እጃቸውን ከዘረጉ በርካታ የጠረፋማ አካባቢ ወገኖችን ለማስተማር እንደሚቻል አስረድተዋል፡፡

በአፍ መፍቻ ቋንቋ ተምሮ ማስተማር ውጤቱ ከፍተኛ በመሆኑም የክርስትናው እምነት ባልተዳረሰባቸው አካባቢዎች በቋንቋቸው በማስተማር ልንደርስላቸው ይገባል ብለዋል፡፡

ሠልጣኞቹ ሥነፍጥረት፣ ትምህርተ ሃይማኖት፣ የቤተክርስቲያን ታሪክ፣ ነገረ ቅዱሳን፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ሥርዓተ ቤተክርስቲያንና የስብከት ዘዴ በሚሉ ርእሶች ትምህርት እንደተሰጣቸው እና ወደ ክልላቸው ሔደው ምን መሥራት እንደሚገባቸው ምክክር እንደተደረገም ለማወቅ ተችሏል፡፡