Aba Entones Gedam.JPG

በዓለማችን የመጀመሪያ የሆነው የአባ እንጦንስ ገዳም በዐሥራ አራት ሚሊዮን ዶላር እድሳት ተደረገለት

ገዳሙ አንድ ሺሕ ስድስት መቶ ዓመታትን አስቆጥሯል

በሻምበል ጥላሁን

በዓለም የመጀመሪያው የምንኩስናና የገዳማውያን ኑሮ መሥራች የሆነው የአባ እንጦንስ ገዳም በግብፅ መንግሥት በዐሥራ አራት ሚሊዮን ዶላር ወጪ እድሳት ተደርጎለት ለአገልግሎት መዘጋጀቱን ቢቢሲ የካቲት 4 ቀን 2002 ዓ.ም ዘገበ፡፡ በግብፅ የሚገኘው የቅዱስ እንጦንስ ገዳም ከአንድ ሺሕ ስድስት መቶ ዓመት በላይ ዕድሜ ያለው ጥንታዊ ገዳም ነው፡፡

Aba Entones Gedam.JPG 

በግብፅ የሚገኘው የአባ እንጦንስ ገዳም 

ገዳሙ ከዕድሜ ብዛት በእርጅና ከደረሰበት ጉዳት ተጠግኖ ለቱሪስት ኢንዱስትሪው ተጨማሪ አቅም እንዲፈጥር የግብፅ መንግሥት ከዐሥራ አራት ሚሊዮን ዶላር በላይ ወጪ እንዳደረገ ዘገባው ጠቁሞ፤ ገዳሙ መንፈሳዊ እሴቱና ታሪካዊ ዳራው እንዳይጠፋ ለማደስ ከስምንት ዓመት በላይ እንደፈጀም የዜና ምንጩ አስታውቋል፡፡

የቢቢሲ ዘገባ እንዳመለከተው፤ የገዳሙ መታደስ የሀገሪቱን የቱሪስት ኢንዱስትሪ ከማስፋፋቱም በላይ ከፍተኛ የኢኮኖሚ አቅም ለመገንባትም እንደሚያስችል አመልክቷል፡፡

በግብፅ ስዊዝ ከተማ የሚገኘው የአባ እንጦንስ ገዳም መታደስ፣ አገልግሎት ላይ መዋልና ለቱሪስት መስህብነት ክፍት መሆኑ፤ ሀገሪቱ የቀድሞ ታሪኳንና ቅርሷን ለመጠበቅ የምታደርገውን ጥረት እንደሚያሳይ ዛሒ ሐዋስ የተባሉት የግብፅ ዋና የቅሪተ አካል ተመራማሪ መናገራቸውንም የዜና ምንጩ አስታውቋል፡፡

ገዳሙ ቅዱስ እንጦንስ በሦስተኛው መቶ ከፍለ ዘመን በቀይ ባሕር አካባቢ በሚገኘው ተራራማና በረሐማ አካባቢ ለጸሎት የመነኑበት ቦታ ነው፡፡

በመልሶ ግንባታው ወቅት በገዳሙ የሚኙት ሁለት አብያተ ክርስቲያናትና ሁለት ማማዎች በጥንቃቄ መንፈሳዊና ታሪካዊ ይዘታቸው ሳይቀየር መሠራታቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡

የቅዱስ እንጦንስ ገዳም በግብፅ ኦርቶዶክሶችም ሆነ በአምስቱ ኦሪየንታል አኀት አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ ታዋቂ ነው፡፡