ማእከለ ክረምት

ዲያቆን ዘክርስቶስ ፀጋዬ

ዘመነ ክረምት የሚጋመስበት ወቅት ማዕከለ ክረምት ይባላል፡፡ በዚህ ክፍል ውስጥ ሁለት  ንኡስ ክፍል ይገኛሉ፤ እነርሱም ዕጒለ ቋዓት እና ደሰያት / ዐይነ ኩሉ/ በመባል ይታወቃሉ፡፡ ይህም ወቅት ከነሐሴ ፲፩ – ፳፯ ቀን ድረስ ያለውን ፲፯ ዕለታት ያካትታል፡፡ ፍጥረታትና በባሕር የተከበቡ ደሴቶች የሚታወሱበት ወቅትም ነው፡፡

ዕጒለ ቋዓት- የሚለው ቃል ቁራን ያመለክታል፤ ቁራ ከእንቁላሉ ተቀፍቅፎ ሲወጣ ያለ ፀጉር በሥጋው ብቻ ይወጣል፡፡ እናትና አባቱም እነርሱን ባለመምሰሉ ደንግጠው ይሸሹታል፤ በዚህ ጊዜ የሚንከባከበው ሲያጣ እግዚአብሔር በረድኤት አፉን ከፍቶ ምግብ ሲሻ ተሐዋስያንን ብር ብር እያደረገ ከአፉ ያስገባለታል፡፡ (ኢዮ. ፴፰፥፵፩) «ለቁራ መብል የሚሰጠው ማን ነው?›› ብሎ እንደገለጸው እግዚአብሔር የሰጠውን እየተመገበ ቆይቶ ሲጠነክር እንደ እናትና አባቱ ያለ ፀጉር ያወጣል፡፡ በዚህ ጊዜ ግን አባቱና እናቱ ቀርበው ይንከባከቡታል፡፡ ቁራ በሥነ ፍጥረት አቆጣጠር በክንፍ ከሚበሩ አዕዋፍ ነው፡፡ ይህም አምላካችን እግዚአብሔር ለፍጥረቱ የሚያስብ በመሆኑ ይህን ዘመን ርኅራኄ ለተመላው ሥራው መታሰቢያ እንዲሆን ቤተክርስቲያን ዕለ ቋዓት በማለት ታስታውሳለች፡፡

ደሰያት – የሚለው ቃል በውኃ የተከበቡ ቦታዎችን ያመለክታል፡፡ እነዚህን ቦታዎች በውኃ እንዲሸፈኑ አድርጎ በውስጣቸው ያሉትን ሰዎች እንስሳት፤ አራዊትና አዕዋፍ ሁሉ የሚጠብቃቸው፣ በተስፋና በእምነት አበርትቶ የሚያኖራቸው እግዚአብሔር ነው፡፡ ስለዚህም ሰዎች እግዚአብሔርን በዚህ ያመሰግኑታል፡፡ ደሴት የቤተክርስቲያን ምሳሌ ናት፤ አንዲት ደሴት በውስጧ ብዙ ፍጥረታትን ትይዛለች፡፡ ከደሴት የተጠጉ ድኅነትን እንደሚያገኙ ሁሉ ወደ ቤተክርስቲያን የተጠጉ ሁሉ ከሞተ ሥጋ ከሞተ ነፍስ ይጠበቃሉ፡፡

በዚህ ዕጒለ ቋዓትና ደሰያት ወቅት ክፍለ ክረምቱ እየተገባደደ፣ ውኃው እየጠራ፣ መሬቱ እየረጋ፣ ደመናውና ጉሙ እየተቃለለ፣ የወንዝ ሙላት እየቀነሰ፣ የክረምት ምግባቸውን ይዘው በየዋሻው የከረሙ ጭልፊቶችና አሞራዎች ድምጻቸውን እየሰሙ ምግብ ፍለጋ ሲወጡ የሚታይበት ወቅት ነው፡፡

‹‹ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት፣ ቡሄ ካለፈ የለም ክረምት›› እንዳለው፤ ዝናብ ይቀንሳል፣ ምድሪቱም መቀዝቀዝና መጠንከር የምትጀምርበት ወቅት ነው፡፡

ቅድስት ቤተክርስቲያን በዚህ ወቅት እግዚአብሔር አምላክ ለሥጋ ሁሉ ምግብን የሚሰጥ ምሕረቱም ለዘላለም የሆነውን የሰማይን አምላክ መሆኑንና ፍጥረታትም ሁሉ እርሱን ተስፋ የሚያደርጉ መሆናቸውን የሚገልጡ መዝሙራት፣ ትምህርት፣ ስብከት ይሰጣል፣ ይነበባል፡፡ (መዝ.፻፵፬፥፲፮-፲፯)

በተጨማሪ በዚህ በማእከለ ክረምት ‹‹ዕረፍተ አበው›› ከነሐሴ ፳፯ እስከ ነሐሴ ፳፱ ድረስ ባለው ጊዜ ይታሰባል፡፡ ከ፳፪ቱ አርዕስተ አበው አብርሃም፣ ይስሐቅና ያዕቆብ የቤተሰቦቻቸው ዕረፍት ይታሰባል፡፡ የአብርሃም ታዛዥነት እና የይስሐቅ ቤዛነት ይታሰባል፡፡ የተቀበሉትም ቃልኪዳን ‹‹ወተዘከረ ሣህሉ ዘለዓለም ዘሠርዓ ለአብርሃም መመሐለ ለይስሐቅ ወዐቀመ ስምዐ ለያዕቆብ ያረኁ ክረምተ ይገብር ምሕረተ እምሰማይ ይሁብ ወእምድር በረከተ ያጸግብ ነፍሰ ርኅብተ›› በማለት ይዘመራል፡፡

ምልአተ ባሕር

ዲያቆን ዘክርስቶስ ፀጋዬ

የበአተ ክረምት ሁለተኛው ክፍል ምልአተ ባሕር ይባላል፡፡ ይህም ከሐምሌ ፲፱ እስከ ነሐሴ ፲ ድረስ ያለው ወቅት ሲሆን ዝናም ምድርን የሚያለመልምበት፤ የተዘራው የሚበቅልበት፤ በፀሐይ ሐሩር የደረቁ ዛፎች ሁሉ የሚያቆጠቁጡበት ወቅት ነው፡፡ በተለይ ከሐምሌ ፲፱ እስከ ሐምሌ ፳፱ መባርቅት የሚበርቁበት፤ ባሕርና አፍላጋት የሚሞሉበት ወቅት ነው፡፡

መብረቅና ነጎድጓድ

መብረቅ ማለት የእሳት ሰይፍ፤ የእሳት ፍላፃ፤ በዝናም ጊዜ ከደመና አፍ የሚመዘዝ የሚወረወር ነው፡፡ (ራእ ፬፥፭፤ ኤር ፲፥፲፫፤ ኢዮ. ፴፯፥፬) የመብረቅ ተፈጥሮ ውሃው በደመና አይበት ተቋጥሮ ሲመጣ በነፋስ ወደል ጋዝ ተጭኖ ፤ ደመናና ደመና በተጋጨ ጊዜ የሚፈጠር ነው፡፡ ወተት ሲገፋ ቅቤ እንደሚወጣው አይነት ማለት ነው፡፡

ነጎድጓድ ማለት ታላቅ ግሩም ድምፅ፤ የሚያስፈራ፤ የሚያስደነግጥና የሚያንቀጠቅጥ ሲሆን (መዝ. ፸፮፥፲፰፤ ኢዮ. ፵፥፬)፤ መብረቅ ከወረደ በኋላ የሚሰማ ድምፅም ነው፡፡ (ኢዮ. ፴፯፥፪-፭፤ መዝ. ፳፰፥፫) ነገር ግን ለማስደንገጥ ወይም ለመዓት ብቻ የተፈጠረ አይደልም፤ ማኅፀነ ምድርን በመክፈት ውኃው ሠርፆ እንዲገባና አዝርዕትና አትክልት እንዲበቅሉ፤ እንዲያብቡና እንዲያፈሩ የሚያደርግ ጭምር ነው፡፡(ሄኖ.፮፥፩)

የክረምትን ኃይልና ብርታት ጥግ አድርገው የሚከሠቱ የተፈጥሮ ኃይላት ዑደትም ይጸናበታል፡፡ መብረቅ፤ ነጎድጓድ፤ ባሕርና አፍላጋት (ወንዞች) ይሠለጥናሉ፡፡ጥልቅ የሆኑ ቦታዎች መጠናቸው ያድጋል፤ ምንጮች ይመነጫሉ፤  የወንዞች ሙላት ይጨምራል፡፡

በቅድስት ቤተክርስቲያን በዚህ ክፍለ ክረምትና ንኡስ ክፍል ዘርዕን፤ ደመናን፤ ዝናምን የሚያዘክሩ እና የመብረቅን፤ የነጎድጓድን፤ የባሕርን፤ የአፍላጋትን፤ የጠልን ጠባይዓት የሚያመለክቱ መዝሙራት ይዘመራሉ፤ ምንባባት ይነበባሉ፤ ስብከት ይሰበካል፡፡

ኢትዮጵያዊ ቅዱስ ያሬድም ይህን ወቅት አስመልክቶ በድጓው ላይ በገለጸው መሠረት ‹‹ደምፀ እገሪሁ ለዝናም ሶበ ይዘንም ዝናም ይትፌሥሑ ነዳያን፤ ይጸግቡ ርኁባን ምድርኒ ርእየቶ ወአእኰተቶ ባሕርኒ ሰገደት ሎቱ፡፡ የዝናም ድምፅ ተሰማ፤ ዝናብም በዘነመ ጊዜ ድሆች ደስ ይሰኛሉ፤ ረኃብተኞችም ይጠግባሉ፤ ምድር አየችው፤ አመሰገነችውም፤ ባሕርም ሰገደችለት›› የሚለው ዜማ ይዜማል፡፡

ቅዱስ ዳዊት ደግሞ በመዝሙሩ ‹‹ዘይገለብቦ ለሰማይ በደመና፤ ወያስተዴሉ ክረምተ ለምድር፡፡ ዘያበቊል ሣዕረ ውስተ አድባር፡፡ ወሐመልማለ ለቅኔ እጓለ እመሕያው፡፡ ‹‹ሰማይን በደመና የሚሸፍን፤ ለምድርም ዝናምን የሚያዘጋጅ፣ ሣርን በተራሮች ላይ ልምላሜውንም ለሰው ልጆች አገልግሎት የሚያበቅል›› (መዝ.፻፵፮፥፰፤መዝ.፻፴፬፥፮፤መዝ.፸፮፥፲፰፤ መዝ.፷፬፥፱) ሲል ዘምሯል፡፡

እግዚአብሔር በነጎድጓድና በመብረቅ፤ በባሕርና በሐይቅ ሁሉ ላይ ሥልጣን ያለው አምላክ መሆኑን፤ የሚታዩና የማይታዩ ፍጥረታት ሁሉ የኃይሉ መገለጫዎች እንደሆኑ የሚያስተምሩ መዝሙራት ይዘመራሉ፡፡ ምንባባትም ከቅዱስ ወንጌልና ከቅዱስ ጳውሎስ መልእክታት እንዲሁም ከሐዋርያት ሥራ ክረምቱን በተመለከተ የተዘጋጁት ይነበባሉ፡፡

 

በአተ ክረምት

 ዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት፣ በሀገራችን ኢትዮጵያ የዘመን አቈጣጠር ስሌት መሠረት ወቅቶች በአራት ይከፈላሉ፡፡ እነዚህም፡- ዘመነ መጸው (መከር)፣ ዘመነ ሐጋይ (በጋ)፣ ዘመነ ጸደይ (በልግ) እና ዘመነ ክረምት ይባላሉ፡፡ ከአራቱ ወቅቶች መካከልም ከሰኔ ፳፮ እስከ መስከረም ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ጊዜ (አሁን የምንገኝበት ወቅት) ዘመነ ክረምት ተብሎ ይጠራል፡፡ ቃሉን ለማብራራት ያኽል፣ ‹ክረምት› የሚለው ቃል ‹ከረመ – ከረመ› ካለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲኾን፣ ትርጕሙም የዝናም፣ የአዝርዕት፣ የአረም ጊዜ፣ እንደዚሁም ዕፀዋት፣ አዝርዕትና አትክልት በቅለው፣ ለምልመው የሚያድጉበት፣ ምድር በአረንጓዴ ዕፀዋትና በልምላሜ የምታሸበርቅበት ወቅት ማለት ነው፡፡ ‹ዘመነ ክረምት› ማለትም ይኼንኑ ወቅት የሚያስገነዝብ ትርጉም አለው፡፡

በአተ ክረምት (ዘርዕ፣ ደመና)

ከሰኔ ፳፮ እስከ ሐምሌ ፲፰ ቀን ድረስ ያለው የመጀመሪያው የክረምት ክፍለ ጊዜ ‹በአተ ክረምት› ወይም ‹ዘርዕ፣ ደመና› ይባላል፡፡ ‹በአተ ክረምት› ማለት ‹የክረምት መግቢያ፣ መጀመሪያ› ማለት ነው፡፡ በዚህ ወቅት በቤተ ክርስቲያናችን ስለ ክረምት መግባት፣ ስለ ዘርዕ፣ ስለ ደመና እና ስለ ዝናም የሚያዘክሩ መዝሙራትና ምንባባት ይዘመራሉ፣ ይነበባሉ፡፡ ይህ ወቅት ደመና ሰማዩን የሚሸፍንበት፣ የዝናም መጠን የሚያይልበትና መሬት በዝናም ረክታ ዘር የምታበቅልበት ጊዜ ነውና፡፡

ዘርዕ

ምድር ከሰማይ ዝናምን፣ ከምድርም ዘርን በምታገኝበት ወቅት ዘሩን አብቅላ ለፍሬ እንዲበቃ ታደርጋለች፡፡ በምድር የምንመሰል የሰው ልጆችም ከእግዚአብሔር ባገኘነው ጸጋ ተጠቅመን፣ ከቅዱሳት መጻሕፍት እና ከመምህራነ ቤተ ክርስቲያን የምናገኘውን ቃለ እግዚአብሔር በተግባር ላይ ማዋል እንደሚገባን ከምድር እንማራለን፡፡ ይህን ካደረግን ዋጋችን እጅግ የበዛ ይኾናል፣ ከዚህም አልፎ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ እንበቃለን፡፡ የተዘራብንን ዘር ለማብቀል ማለትም ቃሉን በተግባር ለማዋል ካልተጋን ግን በምድርም በሰማይም ይፈረድብናል፡፡ ‹‹ምድርም በእርስዋ የሚወርደውን ዝናብ ከጠጣች፣ ያን ጊዜ ስለ እርሱ ያረሱላትን መልካም ቡቃያ ታበቅላለች፡፡ ከእግዚአብሔር ዘንድም በረከትን ታገኛለች፡፡ እሾኽንና ኵርንችትን ብታወጣ ግን የተጣለች ናት፡፡ ለመርገምም የቀረበች ናት ፍጻሜዋም ለመቃጠል ይኾናል፣›› በማለት ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ገለጸው (ዕብ. ፮፥፯-፰)፡፡

በቅዱስ ማቴዎስ ወንጌል ፲፫፥፩-፳፫ እንደ ተገለጸው ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የክርስትና ሕይወትን ከዘርና ፍሬ ጋር በማመሳሰል አስተምሯል፡፡ ይኸውም አንድ ገበሬ ዘር ሲዘራ በመንገድ ዳር የወደቀው ዘር ከመብቀሉ በፊት በወፎች እንደ ተበላ፣ በጭንጫ ላይ የተጣለውም ወዲያውኑ ቢበቅልም ነገር ግን ሥር መስድድ አልቻለምና፡፡ በፀሐይ ብርሃን እንደ ጠወለገ፤ በእሾኽ መካከል የወደቀው ደግሞ ሲበቅል በእሾኽ እንደ ታነቀ፣ ከሁሉም በተለየ መልኩ በመልካም መሬት ላይ የተጣለው ዘር ግን አድጎ መቶ፣ ስድሳ፣ ሠላሳ ፍሬ እንደ ሰጠ የሚያስረዳ ነው፡፡

ይህም ምሳሌ አለው፡፡ ጌታችን ለደቀ መዛሙርቱ እንደ ተረጐመው በመንገድ ዳር የተዘራው ዘር የእግዚአብሔርን ቃል ሰምቶ የማያስተውል (ልብ የማይል) ክርስቲያን ምሳሌ ነው፣ እንደዚህ ዓይነቱ ምእመን ሙሉ እምነት ስለማይኖረው በመከራው ጊዜ አጋንንት ድል ያደርጉታል፡፡ በጭንጫ ላይ የተዘራው ደግሞ ቃሉን ሰምቶ ወዲያው በደስታ የሚቀበል፣ ነገር ግን ተግባራዊ የማያደርግ (የማይተገብር) የክርስቲያን ምሳሌ ነው፡፡ ይህ ምእመንም በጠንካራ እምነት ላይ የጸና አይደለምና በሃይማኖቱ ምክንያት መከራ ወይም ስደት በደረሰበት ጊዜ ፈጥኖ ይክዳል፡፡ በእሾኽ መካከል የተዘራውም ቃሉን የሚሰማ ቢሰማም ግን በዚህ ዓለም ዐሳብና ባለ ጠግነት ተታሎ ቃሉን የማይተገብር ክርስቲያን ምሳሌ ነው፡፡

በመልካም መሬት የተዘራው ደግሞ ቃሉን ሰምቶ ተግባር ላይ የሚያውል ክርስቲያን ምሳሌ ነው፡፡ እንደዚህ ዓይነት ምእመን በተማረው ትምህርት ጸንቶ ይኖራል፣ መልካም ሥራም ይሠራል፡፡ በመልካም መሬት የተዘራው ዘር ስለ አንዱ ፋንታ መቶ፣ ስድሳ፣ ሠላሳ እንደሚያፈራ ሁሉ በክርስቲያናዊ ግብር ጸንቶ የሚኖር ምእመንም ሥራውን በሦስት መንገድ ማለትም በወጣትነት፣ በማእከላዊነትና በፍጹምነት ደረጃ እንደሚፈጽም፣ ዋጋውንም በሥራው መጠን እንደሚያገኝ የሚያስረዳ ነው፡፡ በሌላ በኩል ባለ መቶ ፍሬ የሰማዕታት፣ ባለ ስድሳ የመነኮሳት፣ ባለ ሠላሳ በሕግ ተወስነው በዓለም የሚኖሩ ምእመናን ምሳሌ ነው፡፡ በተመሳሳይ ምሥጢር ሁሉም የፍሬ መጠን በሁሉም ጾታ ምእመናን ሕይወት ውስጥ እንደሚገኝ የትርጓሜ ሊቃውንት ያስተምራሉ፡፡ ስለዚህም በሰማዕትነትም፣ በምንኵስናም፣ በዓለማዊ ሕይወትም ውስጥ የሚኖሩ ምእመናን መልካም ግብራቸው እጅግ የበዛ ከሆነ በባለ መቶ ፍሬ፣ መካከለኛ ከሆነ በባለ ስድሳ፣ ከዚህ ዝቅ ያለ ከሆነ ደግሞ በባለ ሠላሳ ፍሬ ይመሰላል፡፡ (ትርጓሜ ወንጌለ ማቴዎስ፣ ማቴ. ፲፫፥፩-፳፫)፡፡

ደመና

እግዚአብሔር አምላካችን የውቅያኖስ እና የሐኖስ ድንበር ይሆን ዘንድ በውኃ መካከል ጠፈርን ፈጥሮ ከጠፈር በታች (በዚህ ዓለም) ያለው ውኃ በአንድ ቦታ እንዲወሰን አድርጎታል፡፡ ከዚያም ከምድር እስከ ብሩህ ሰማይ ድረስ የነበረውን ውኃ ከሦስት ከፍሎ ሢሶውን አርግቶ ጠፈር ብሎ ሰይሞታል፡፡ ከጠፈር በላይ ያለውን ሢሶውን የውኃ ክፍል ሐኖስ ብሎታል፡፡ ሢሶውንም ይህንን ዓለም ከሰባት ከፍሎ ሰባተኛውን ዕጣ አጐድጕዶ በዚያ ወስኖ ስሙን ውቅያኖስ ብሎ ጠርቶታል፡፡ የብሱን ክፍል ደግሞ ምድር ብሎ ሰይሞታል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ከደረቅ ምድር ደረቅ ጢስን፣ ከርጥብ ባሕር ርጥብ ጢስን አስወጥቶ እንደ ጉበት በለመለመች ምድር ላይ ደመናን አስገኝቷል (ትርጓሜ መዝሙረ ዳዊት፣ መዝ. ፻፴፬፥፯)፡፡

ደመና፣ ዝናምን የሚሸከም የማይጨበጥ፣ የማይዳሰስ ጢስ መሰል ፍጥረት ነው፡፡ በትነት አማካይነት፣ በደመና ተሸካሚነት ከውቅያኖሶች እና ከወንዞች እየተቀዳ ወደ ሰማይ ተወስዶ እንደ ገና ተመልሶ ወደ ምድር የሚጥለው ውኃ ዝናም ይባላል፡፡ ይኸውም በእግዚአብሔር ጥበብ በደመና ወንፊትነት ተጣርቶ ለፍጡራን በሚመችና በሚጠቅም መጠን በሥርዓት ይወርዳል፡፡ ‹‹ያጸንዖ በፍኖተ በድው ከመ ይዝንም ብሔረ ኀበ አልቦ ሰብእ ወኢይነብሮ ዕጓለ እመሕያ፣ ዝናሙን ሰው በሌለበት በምድረ በዳ ያዘንመዋል፤›› እንዳለ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ በቅዳሴው፡፡ ይህ ኃይለ ቃል እግዚአብሔር በረዶውን በምድረ በዳ አፍስሶ የጠራውን ውኃ ሰው ወዳለበት እንዲዘንም ማድረጉን የሚያስረዳ መልእክት የያዘ ሲሆን፣ ምሥጢሩም ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንበለ ዘርዐ ብእሲ (ያለ ወንድ ዘር) በልዩ ጥበቡ ተፀንሶ ከቅድስት ድንግል ማርያም መወለዱንና በተዋሐደው ሥጋ በምድር ተመላልሶ ወንጌልን ማስተማሩን፣እንደዚሁም ‹‹ሑሩ ወመሀሩ፤ ሒዱና አስተምሩ›› ብሎ ቅዱሳን ሐዋርያትን በመላው ዓለም ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት ማሰማራቱን ያመለክታል (ትርጓሜ ቅዳሴ ኤጲፋንዮስ፣ ፪፥፭-፮)፡፡

ዘመነ ክረምት ስለ ሥነ ፍጥረት ዘርዘር ባለ መልኩ የሚነገርበት፤ ፍጡርን ከፈጣሪ መናን (ምግብን) ከተመጋቢ ለይቶ የሚያሳይ እና የሚያሳውቅ ዘመን ነው፡፡ በዚህ ወቅት የውኃ ባሕርይ ይሠለጥናል፣ ውኃ አፈርን ያጥባል፣ እሳትን ያጠፋል፡፡ ሆኖም ግን ውኃ በብሩህነቱ ከእሳት፣ በቀዝቃዛነቱ ከነፋስ፣ በእርጥብነቱ ከመሬት ጋር ተስማምቶ ከሦስቱ ባሕርያት ጋር ይኖራል፡፡ ይህን ምሥጢር ከሕይወታችን ጋር አያይዘን ስንመለከተው ዘመነ ክረምት የክርስትና ምሳሌ ነው፡፡ በክረምት ወቅት ገበሬው ብርዱንና ዝናሙን ሳይሳቀቅ ለሥራ ይሰማራል፣ በበጋው የእጁን ፍሬ ያገኝ ዘንድ የክረምቱን መከራ ይታገሣል፡፡ ይህም ምእመናን በሰማያዊው ዓለም የምናገኘውን ተድላና ደስታ በማሰብ በምድር ቆይታችን ወቅት የሚደርስብንን ልዩ ልዩ መከራ በትዕግሥት ማሳለፍ እንደሚገባን ያስገነዝባል፡፡

በዘመነ ክረምት አዝርዕቱ በስብሰው ከበቀሉ፣ ካበቡና ካፈሩ በኋላ የሚጠቅሙት በሪቅ፣ በጎተራ እንደሚሰበሰቡ፣ እንክርዳዶቹ ደግሞ በእሳት እንደሚቃጠሉ ሁሉ እኛም ተወልደን፣ ተጠምቀን፤አድገን፣ ዘራችንን ተክተን እንደምንኖር፣ ዕድሜያችን ሲያበቃም እንደምንሞት፣ ሞተንም እንደምንነሣና መልካም ሥራ ከሠራን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እንደምንገባ፣ በኀጢአት ከኖርን ደግሞ በገሃነመ እሳት እንደምንጣል የምንማርበት ወቅት ነው፡፡ በመሆኑም ሰይጣን በሚያዘንበው የኀጢአት ማዕበል እንዳንወሰድና በኋላም በጥልቁ የእሳት ባሕር እንዳንጣል ዅላችንም ቅዱሳት መጻሕፍትና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያዘጋጁልንን የቃለ እግዚአብሔር ዘር በእርሻ ልቡናችን በመዝራት (በመጻፍ) እንደየዓቅማችን አብበን፣ ያማረ ፍሬ አፍርተን መንግሥቱን ለመውረስ መዘጋጀት ይኖርብናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ክርስቲያናዊ ሕይወት

ዲያቆን ዮሴፍ በቀለ

በክርስቲያናዊ ሕይወት ውስጥ መልካም ሥራ ሁልጊዜ ይኖራል፤መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ   በትምህርተ ወንጌል እንዳስተማረን  ድኅነትን የምናገኝው በሕገ እግዚአብሔር ጸንተን ስንኖር እንደሆነ ነግሮናል። የሰው ሕይወቱ የጸጋ ነው፤ በፈቃዱ በሁለት ሞት ነፍሱን/ሕይወቱን/ ይነጠቃል፡፡ የመጀመሪያው ሞት የማይቀር ሲሆን የሁለተኛው ሞት ግን በሕገ እግዚአብሔር ለልደተ ነፍሳት የተሰጠ ነው፤ ራዕ. (፪፥፲፩)፤ ሕያው የሆነ ሰው እንጂ ሕይወት የሆነ ሰው የለምና፡፡

ስለሆነም ለዘለዓለም በሕይወት ለመኖር ይቻለን ዘንድ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምድር ላይ በቆየበት ጊዜ ያደረገውን ተአምር፤ ያስተማረውን ወንጌልና  ለእኛ የገለጸልንን ፍቅር መሠረት አድርገን መመራት ይጠበቅብናል። ይህንንም በተግባር ለመፈጸም የሚከተሉትን ምግባሮች ማከናወን አለብን፡፡

፩.አገልግሎት

ከሁሉም አስቀድሞ የሰው ልጅ ዕለት ዕለት ፈጣሪውን ሊያመሰግን ይገባል፤ ይህም መጸለይ፤መጾም፤ማስቀደስና መዘመር ይገባዋል፡፡ ከዚህም ባሻገር ነዳያንን ማብላትና ማጠጣት በጉልበትና በሙያ አድባራትን ማሰራት ከአንድ ክርስቲያን የሚጠበቅ ሲሆን አሁን አሁን ግን የምንመለከተው እንደዚህ አይደለም፡፡ የዛሬ ፲ ዓመት ሰንበት ተማሪ የነበረው ልጅ ከዓመት በኋላ የመድረክ ዘፋኝ ይሆናል፤ የዛሬ ፭ ዓመት ሰንበት ትምህርት ቤት ድራማ ይሰራ የነበረው ሰው በኋላ ተለውጦ ሌላ ታሪክ ውስጥ ይገባል፡፡ የሰንበት ትምህርት ቤት ሰብሳቢ፤ ጸሓፊና አባል የነበረው፤ ሚስት ሲያገባ ያንን ሁሉ እርግፍ አድርጎ ይተወዋል፤ ትዳር እኮ የአገልግሎት ጡረታ አይደለም፤ አንዴ ካገቡ አይመለሱም፡፡

ሰንበት ተማሪ ሆኖ ቤተክርስቲያንን እያገለገለ እስከ ሕይወቱ መጨረሻ ዘማሪ፤ ካህን፤ ዲያቆን ወይም ሰባኪ ሆኖ ገዳማትን እያሰራ፤ ነዳያንን እያበላ፤ ጉባኤ እያዘጋጀ፤ ጽዋ ማኅበራትን እየመራና ወዲህ ወዲያ ሳይል፤ ታመምኩ፤ ተቸገርኩ፤ ምስጋና ቢስ ነኝ፤ እጄን በቆረጠው ሳይል የሚኖር ማን ነው? አንዳንዶች ደከምን ብለው አገልግሎትን  የሚተው አሉ፡፡ ታማን ብለን የምንተውም አለን፤ ይህቺን ካልታገስን ታዲያ ስለ ዲዮቅልጥያኖስ ዘመን ለምን እናወራለን? እስከ መጨረሻው የትኛው ሰው ነው የሚጸናው? በክርስቲያናዊ ሕይወት እስከ መጨረሻዋ ዕለት መጽናት ያስፍልጋል፡፡

.ጊዜን ማክበር

ጊዜ ከእግዚአብሔር የተሰጠን ስጦታ ነው፤ እናም በአግባቡ ልንጠቀምበት ያስፈልጋል፡፡ ጉባኤ ላይ በመገኘት፤ ሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ በማገልገል፤ ድሆችን በመጎብኘት፤ ሕመምተኞችን በመጠየቅ፤ ገዳማትንና አድባራትን ለማሰራት በመድከም፤ መምህራኑ ሲያስተምሩና መዘምራኑ ሲዘምሩ በማገልገል ጊዜን ማክበር ያስፈልጋል፡፡ በማቴዎስ ወንጌል  (፳፭፥፴፬-፴፮) ላይ እንደተገለጸው «እናንተ የአባቴ ቡሩካን፤ ዓለም ሳይፈጠር የተዘጋጀላችሁን መንግሥት ትወርሱ ዘንድ ኑ። ተርቤ አብልታችሁኛልና፤ተጠምቼም አጠጥታችሁኛልና፤ እንግዳም ሆኜ ተቀብላችሁኛልና፡፡ ታርዤ አልብሳችሁኛልና፤ ታምሜም ጎብኝታችሁኛልና፤ ታስሬም ወደ እኔ መጥታችሁ  ጠይቃችሁኛልና» ይለናል።

መጠቀም ያለብን ትርፍ ጊዜያችንን አይደለም፤ ያለንን ጊዜ መስጠትና ሙሉ ጊዜን መስጠት ይለያያሉ፤ በወንጌል እንደተጠቀሰው አንድ ሰው ከሞላው ከኪሱ አፈሰና ሰጠ፤ አንዲት  ምስኪን መበለት ደግሞ ሁለት ሳንቲም ነበራትና እሱን ሰጠች፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእነዚህ ሰዎች ሁሉ ይህቺ ጸደቀች አለ፡፡ በሉቃስ ወንጌል (፳፩፥፫-፬) ላይ እንደተናገረው «እውነት እላችኋለሁ፥ይህቺ ደሃ መበለት ከሁሉ ይልቅ አብዝታ ለእግዚአብሔር መባ አገባች፡፡ እነዚህ ሁሉ ከተረፋቸው ለእግዚአብሔር መባ አግብተዋና፤ ይህች ግን ከድህነቷ ያላትን ጥሪቷን ሁሉ አገባች»፡፡ካለን እንድንሰጥ ነው እንጂ ሲተርፈን፤ ሥራ ሠርተን፤ በልተን፤ ጠጥተን፤ተዝናንተን ስንጨርስ መጨረሻ ላይ የት ልሂድ ብለን ቤተክርስቲያን የምንሄድ ከሆነ ይህ ለጊዜ ዋጋ መስጠት አይደለም፡፡ በጊዜያችን ተጨማሪ ልንሰራበት የምንችለውንና ገንዘብ የምናገኝበትን፤ ሰው ቤት ሄደን ጥዑም ምግብ ተመግበን የምንጠጣበትን ጊዜ ሰውተን፤ እንደ አስፈላጊነቱ ስንሰጥ ለጊዜ መሥዋዕት አደረግን ይባላል፤ሲተርፍ መስጠት ዋጋው ትንሽ መሆኑን ወንጌልም ነግሮናልና፡፡

፫. በሃይማኖት መጽናት

በዮሐንስ ራእይ ፲፪፥፲፮-፷ እንደተጠቀሰው ዘንዶው በሴቲቱ ላይ ተቆጥቶ የእግዚአብሔርን ትእዛዛት የሚጠብቁትን የኢየሱስ ምስክር ያላቸውን ከዘሯ የቀሩትን ሊወጋ ሄደ ይላል፡፡ ከዘሯ የቀረነውን የኢየሱስ ክርስቶስ ምስክርነት ያለንን ሊዋጋ ከተነሣው ዘንዶ ጋር ታግሎ ሃይማኖትን መጠበቅ ተገቢ ነው፤ በዚህ ዘመን ሃይማኖት ጸንቶ ሃይማኖትን መጠበቅና ከመናፍቃን ጋር መዋጋት የክርስቲያን ኃላፊነት ነው፤ ይሁዳ (፩፥፫) «ለቅዱሳን የተሰጠችውንም ሃይማኖት ትጋደሉላት ዘንድ አማልዳችኋለሁ» ይላል።

ስለ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መጋደል ክርስቲያናዊ ምግባር ነው፤ ብዙዎቹ ዛሬ በገንዘብና ከንቱ በሆነ ነገር ይታለላሉ፤ ቅዱስ ጳውሎስ እንደተናገረው «ለዚህ ዓለም ስሕተት፥ በክርስቶስ ሕግ ያይደለ፥ በሰው ሠራሽ ሥራዐት ለከንቱ የሚያታልሉ ሰዎች በነገር ማራቀቅ እንዳያታልሉአችሁ፥ተጠንቀቁ» (ቈላ. ፪፥፰)፡፡ በሰይጣን በመታለል ሃይማኖታቸውን የሚለውጡ አሉ፤ ጌታችን በማቴ. (፳፬፥፲፫) ላይ «እስከ መጨረሻው የሚታገሥ ግን እርሱ ይድናል» ብሏል፡፡

፬.እራሳችንን ከፍትወት መጠበቅ

 ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ በዚህ ዘመን ራሳችን ከዚህ ዓለም ፍትወት መጠበቅ  እንዳለብን አሳስበለዋል፡፡ አሁንኮ እስከ ጋብቻ ድረስ በድንግልና መጽናት ከባድ ሆኖብናል፤ የ «መ» ሕጎች እየተባለ በትምህርት ቤቱ ሁሉ መከራ የሚበላው ይህን ሕግ እየረሳን ነው፡፡ ልክ የዚህን ዓለም ፍትወት መቻል በእሳት ውስጥ ማለፍ እንደሆነ፤ ፍትወት ራሱን የቻለ እሳት ነው፤ እሳት እንኳን የቀረበውን የራቀውን ይጠራል፡፡ አባቶቻችን «እሳት ይጠራል»  ይላሉ፤ እኛ የምንኖረው በዓለም ነው፡፡ ስለዚህ ለምን በኅሊናችን የፍትወት ስሜት መጣ? ለምን በዙሪያችን ኃጢአት ኖረ? ማለት አንችልም፤ ግን ወንዙን አቋርጠን ማለፍ እንችላለን፤  ራስን በንጽሕና መጠበቅም አለብን፡፡ ወንድና ሴት ራሳቸውን ከዝሙት ስሜት ጠብቀው ሲኖሩ፤ በቤተክርስቲያን በተክሊል ሲጋቡ አክሊል ይጫንላቸዋል፤ ቤተ ክርስቲያን አክሊል ላደረገችለት ሰው ደግሞ እግዚአብሔር እጥፍ ዋጋን እንደሚከፍል ቅዱሳት መጻሕፍት ላይ ተጽፏል፡፡ እነዚህ ሰዎች እድል ወይም ምድራዊ ጥቅም ሳይኖራቸው ቀርቶ አይደለም፤ ነገር ግን ምድራዊ ፍላጎታቸውን በመግታት ከራሳቸው፤ ከጓደኞቻቸውና ከአካባቢያቸው ጋር በመታገል ለነፍሳቸው መሥዋዕት ለመክፈል ስለሚሹ ነው፡፡

፭. በትዳር መጽናት

 በክርስቲያናዊ ሕይወት ውስጥ አንድ ወንድ በአንዲት ሴት፤ አንዲት ሴት በአንድ ወንድ ጸንተው ይኖራሉ፡፡ ባልና ሚስት በመቻቻል በሰላም መኖር ከቻሉ፤ ሰው የራሱን፤ የአጋሩንና የልጆቹን ጠባይ ችሎ በትዕግሥት ከኖረ፤ ሥጋ ወደሙን ተቀብሎም፤ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን  እግዚአብሔርን የሚያገለግል ከሆነ ክርስቲያን ይባላል፡፡ በምንኩስና ሳይወሰኑ ወይም በትዳር አንድ ሳይሆኑ እንዲሁ የሚኖሩ ሰዎች ክርስቲያናዊ ሕይወትን የማይሹ ሰዎች ናቸው፤ ልክ በዘመነ ሰማዕታት ጊዜ እንደነበሩ ለጊዜው ክደናል እንደሚሉት አይነት ናቸው፡፡ ፶ እና ፷ ዓመት በትዳር እየኖሩ የብር፤ የወርቅ፤ የአልማዝና ኢዩቤልዩ የሚያከብሩ ሰዎች ተመችቷቸው እንዳይመስለን፤ ብዙ የችግር ጊዜን አሳልፈው ሊሆን ይችላል፤ እግሬን በሰበረው፤ ምላሴን በቆረጠው፤ አይኔን በሰወረው፤ ብር ብዬ በጠፋው ያሉበት ጊዜም ይኖራል፤ ግን ያን ሁሉ አልፎ መጽናት ያስፈልጋል፡፡

በትዳር ያላችሁ እስከመጨረሻው እንድትጸኑ፤ንጽሕናችሁን ጠብቃችሁ በመዘምርነት የምታገለግሉ፤ በስብከት፤ ለአድባራትና ገዳማት ያላችሁን እየመጸወታችሁ ከቁርሳችሁ ቀንሳችሁ፤ ሁለት ጫማ ካላችሁ አንድ ጫማ፤ ሁለት ልብስ ካላችሁ አንዱን እየለበሳችሁ፤ እኛ ይቅርብን፤ አባቶቻችን ተርበው ከተማ ለከተማ ሲንከራተቱ አንይ ብላችሁ የምታገለግሉ፤ የምታስታርቁ አባቶች፤ የጠፉትን ፈልጋችሁ የምታመጡ፤ መናፍቃንን ተከራክራችሁ የምታሳምኑ፤ አሕዛብን ወደ ጥምቀት የምታመጡ ሰዎች ሁሉ እስከ መጨረሻው ጸንታችሁ፤ ጸንተን፤ ኑ «የአባቴ ብሩካን ዓለም ሳይፈጠር የተዘጋጀላችሁን ርስት ውረሱ» እንድንባል የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፤አሜን፡፡

የዐዋጅ አጽዋማት

በተክለሐዋርያት

የዐዋጅ አጽዋማት በቤተክርስቲያን ለምእመናን ሁሉ አሳውቆ በአንድነት የሚጾም ጾም ነው፤ በሰባትም ይከፈላል፤ እነርሱም የነቢያት  ጾም፤ ጾመ ገሃድ ወይም ጋድ፤ ጾመ ነነዌ፤ የዐብይ ጾም፤ጾመ ድኅነት፤ የሐዋርያት ጾም እና ጾመ ፍልሰታ ናቸው፡፡ በጾም ወቅት ከአንድ ምእመን የሚጠበቁ ምግባራት ደግሞ የሚከተሉት ናቸው፡፡

ሀ. ዕለት ዕለት አብዝቶ መጸለይ

በጾም ወቅት ልናዘወትራቸው ከሚገቡን ምግባራት መካከል ጸሎት አንዱ ነው፤ በጸሎት ያልታገዘ ጾም ከንቱ ነው፤ ኦርቶዶክሳዊ ምእመን በጾም ወቅትና ከጾም ወቅት ውጪ በጸሎት ትጉ መሆን ክርስቲያናዊ ግዴታው ነው፡፡ ጸሎት ከፈጣሪ የምንገኛኝበት ክርስቲያናዊ ምግባር ነው፡፡ ጸሎት ወደ ፈተና እንዳንገባ የሚረዳን የጽድቅ መሥመር ነው፡፡ ‹‹እግዚአብሔርን በጠራሁት ጊዜ ጽድቄን ሰማኝ ጭንቀቴንም አራቀልኝ ይቅር አለኝ ጸሎቴንም ሰማኝ››(መዝ.፬፥፩)

ለ. ከዝሙት መከልከል

ዝሙት ነፍስና ሥጋን ይጎዳል፤ በሰማይም በምድርም ከፍተኛ ቅጣትና ሥቃይን ያመጣል፡፡ ሴሰኝነት መልካም ስምን ያጠፋል፤ ክብርን ያሳጣል፤ ኅሊናን ይበጠብጣል፤ ከዚህ የሚከፋው ደግሞ ከእግዚአብሔር አንድነት የሚለይ መሆኑ ነው፡፡ ሴሰኞችና አመንዝራዎች ከእግዚአብሔር ዘንድ ፍርድ ይደረግባቸዋል፡፡ ነቢዩ ‹‹ወንዶችም ደግሞ ከአመንዝሮች ጋር ይጫወታሉና፥ ከጋለሞቶችም ጋር ይሠዋሉና ሴቶች ልጆቻችሁ በሰሰኑ ጊዜ፥ ሙሽሮቻችሁ በአመነዘሩ ጊዜ አልቀጣኋቸውም፤ የማያስተውልም ሕዝብ ከአመንዝራ ጋር ይቀላቀላል፡፡ (ሆሴ.፬፥፲፬)

ሐ. የስሜት ሕዋሳትን ማስገዛት

በጾም ወቅት ሁሉንም የስሜት ሕዋሳቶችን መግዛት መቻል አለብን፡፡ የስሜት ሕዋሳትን መግዛት ካልቻልን በምኞትና በፍትወት ገመድ እየጎተቱ ወደ ኃጢአት ይወስዱናል፡፡ ለዚህም ነው ሊቁ ቅዱስ ያሬድ በድጓው ይጹም ዓይን (ዓይን ይጹም) ፤ ይጹም ልሳን(አንደበት ይጹም)፤ዕዝንኒ ይጹም እምሰሚዐ ሕሱም (ጆሮም ክፉን ከመስማት ይጹም)፤ በማለት ያስተማረን ዓይን የሚያየውን ጆሮም የሚሰማውን አንደበትም የሚናገረውን ክፉ ነገር አእምሮ ወደ ሐሳብ በመቀየር ወደ ኃጢአት ሊያመራን ይችላል፡፡ በመሆኑም በጾማችን ወይም በክርስትናችን ዓይናችንን ክፉ ነገርን ከማየት አንደበታችንን ክፉን ከመናገር ጆሮአችንንም ክፉን ከመስማት ልንከለክል ይገባናል፡፡ ‹‹ኃጢአትን ወደ መውደድ አንተን ከሚስቡህ ከማየት ከመስማት ተጠበቅ›› (ማር ይስሐቅ)፡፡ ዓለሙንና በዓለም ያለውን አትውደዱ ዓለሙን የሚወድ ግን የአብ ፍቅር በእርሱ የለም በዓለም ያለው ሁሉ እርሱም የሥጋ ምኞትና የዓይን አምሮት ስለገንዘብም መመካት ከዓለም እንጂ ከአብ አይደለም፡፡ (፩ዮሐ.፪፥፲፭‐፲፮)

መ. ቅዱሳት መጻሕፍትን መመርመር ፤ መመልከት

ቅዱሳት መጻሕፍት የሰው ልጅ የፈጣሪውን የእግዚአብሔርን ሕግና ሥርዓት ይማርባቸው ዘንድ የተሰጡትና ከአለማወቅ ወደ ማወቅ ከሞትም ወደ ሕይወት የሚወስዱት የሚያደርሱት ከፈጣሪው ጋርም እንዴት መኖር እንደሚገባው የሚያስተምሩት የቅድስናው መሠረቶች የክርስትና ሕይወት መመሪያዎች ናቸው፡፡ ለዚህም ነው የእግዚአብሔር ቃል ‹‹መጻሕፍትን ካለማወቃችሁ የተነሣ ትስታላችሁ›› በማለት ያስተማረን ቅዱሳት መጻሕፍት እንዴት መጾም እንዳለብን በጾማችን ወቅት ምን ምን ተግባራትን ማድረግ እንዳለብንና እንደሌለብንም ጭምር ያስተምሩናል በጾም የተጠቀሙ የቅዱሳን አባቶቻችንንም ታሪክ እየነገሩን እኛም እንድንጾም ያደርጉናል፡፡

በመሆኑም ኦርቶዶክሳውያን  ምእመናን በጾም ወቅት እነዚህን ቅዱሳት መጻሕፍትን አብዝቶ በማንበብ ወደ ቅድስና ሕይወት የሚወስዱ የእግዚአብሔርን ሕግና ትእዛዛትን መረዳትና መፈፀም ተገቢ ነው፡፡

ሠ. ምጽዋትን ማዘውተር

ምጽዋት ማለት መስጠት፤መለገስ ማለት ነው፡፡ ይህም ከጾም ጋር ከሚተባበሩ ክርስቲያናዊ ምግባራት አንዱ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ድሆችን እናስብ ዘንድ ብቻ ለመኑን ይህንም ላደርግ ደግሞ ተጋሁ›› በማለት እንዳስተማረን ምጽዋት ለምእመናን ትጋት ናት፡፡ (ገላ.፪፥፲)

ምጽዋት መስጠት ከገንዘብ ከዕውቀት ከንብረት…ላይ ለእግዚአብሔር ቤት መለገስ ነው፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአንቀጸ ብፁዓን ትምህርቱ “ብፁዓን መሐርያን የሚምሩ ብፁዓን” ናቸው ያለውን ሊቃውንት ለምጽዋት ሰጥተው ሲተረጉሙት በሦስት መንገድ ያስቀምጡታል፡፡ እነዚህም፡-

.ምሕረት ሥጋዊ፡ ይህ የሚያስረዳው ለሥጋ የሚኾን ነገርን መለገስን ሲኾን
. ምሕረት መንፈሳዊ፡ በምክር በትምህርት ሥነ ልቡናን የሚያንጽ (የሚያበረታታ) ማድረግን ነው፡፡

. ምሕረት ነፍሳዊ፡ ደግሞ «መጥወተ ርእስ» ወይም ራስን እስከ መስጠት መድረስን ነው፡፡ (ማቴ.፭፥፯ትርጓሜ ወንጌል)

ምጽዋት ካለን ነገር ላይ ማካፈልን ያመለክታል፡፡ ለፍጹምነትም የሚያበቃ ምግባር መኾኑ የተመሰከረለት ነው፡፡ «ፍጹም እንድትኾን ለድኻ ስጥ» እንዲል (ማቴ.፲፱፥፳፩) እንደዚሁም «የሚሰጥ ብፁዕ ነው» የሚለው ኃይለ ቃል የሚያስረዳን ይህንኑ ነው፡፡ (ሐዋ.፳፥፴፭) በዕለተ ምጽአትም ከሕይወት ቃል አንዱ በምጽዋት የሚገኝ መኾኑ እሙን ነው፡፡ (ማቴ.፳፭፥፴፭) ምጽዋት በልብስ በገንዘብ እንጀራ በመቁረስ የመሳሰሉትን ለደኃ በመስጠት ለድሆችና ለጦም አዳሪዎች ማካፈል ነው፡፡ በኢየሩሳሌም የሚኖሩ ምእመናን ሀብታቸውን ለደኃ ያካፍሉ ነበር፡፡ (ሐዋ.፬፥፴፪፣፮፥፩) እንደዚሁም ዕውቀትን ማካፈል ምክር መለገስ ከምጽዋት የሚቈጠር ሲኾን ለእግዚአብሔር ቤትም በገንዘብ በጉልበትና በስጦታችን ማገልገል የምጽዋትን ዋጋ ያስገኛል (ዘዳ. ፲፭፥፲፩‐፲፭፤ኢሳ.፶፰፥፯፤፯፤ምሳ.፫፥፳፯፤ሮሜ.፲፪፥፰) እንግዲህ በጾማችን ለኃጢአታችን ሥርየትን፤ ምሕረትና ይቅርታን የምናገኝባቸውን የሥጋና የነፍስ በረከትንም የምንታደልባቸውን እነዚህን ክርስቲያናዊ ምግባራት በሕይወታችን አዘውትረን ልንፈጽማቸው ይገባናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

 

‹‹ጾም የነፍስን ቊስል ትፈውሳለች›› (ቅዱስ ያሬድ)  

                                                                                              በብዙአየሁ ጀምበሬ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ከሚከናወኑ ዓበይት ክርስቲያናዊ ምግባራት መካከል ጾም አንዱና ዋነኛው ነው፡፡ ጾም ‹‹ጾመ››  ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም ተከለከለ፤ተወ፤ታቀበ፤ታረመ ማለት ነው፡፡ በሱርስትና በዕብራይስጥ ቋንቋዎች ‹‹ጻም›› ሲባል በአረብኛ ቋንቋ ደግሞ ‹‹ጻመ›› በመባል ይታወቃል፡፡ (ጾም እና ምጽዋት ገጽ ፰)

የቤተ ክርስቲያናችን የሕግና የሥርዓት መጽሐፍ የሆነው ፍትሐ ነገሥት ደግሞ በአንቀጽ ፲፭ ላይ ‹‹ጾምሰ ተከልኦተ ብእሲ እመብልዕ በጊዜ ዕውቅ በውስተ ሕግ፤ ጾምስ በታወቀው ዕለት፤በታወቀው ሰዓት ከምግብ መከልከል ነው›› በማለት ጾምን በዚህ መልኩ ይተረጕመዋል፡፡

እንግዲህ በሃይማኖታዊ ትርጉሙ ጾም ማለት ራስን ከእህል፤ከውኃ ብሎም አምላካችን እግዚአብሔር ከሚጠላቸው እኩይ ምግባራት ሁሉ ራስን በመከልከል የሥጋን ፈቃድ ለነፍስ በማስገዛት መቆየት ማለት ነው፡፡‹በዚያም ዐርባ ቀንና ዐርባ ሌሊት በእግዚአብሔር ፊት ነበረ፤ እንጀራም አልበላም፤ ውኃም አልጠጣም፤ በጽላቱም ዐሥሩን የቃል ኪዳን ቃሎች ጻፈ።›› (ዘፀ.፴፬፥፳፰) ሁለቱን የድንጋይ ጽላት፥ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር የተማማለባቸውን የቃል ኪዳን ጽላት፥ እቀበል ዘንድ ወደ ተራራ በወጣሁ ጊዜ፥ በተራራው ዐርባ ቀንና ዐርባ ሌሊት ተቀምጬ ነበር እንጀራ አልበላሁም፥ ውኃም አልጠጣሁም›› ተብሎ እንደተጻፈ። (ዘዳ.፱፥፱)

ከዚህም ባሻገር ጾም ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ ‹‹ጉልበቶቼ በጾም ደከሙ፤ ሥጋዬም ቅባት በማጣት ከሳ›› በማለት እንደናገረው በዚህ የጾም ወቅት ከጥሉላት መባልዕት ወይም የእንስሳት ተዋጽኦ የሚባሉትን ማለትም እንደ ሥጋ፤ወተት፤ዕንቁላል፤ዐይብ፤ ቅቤ ወዘተ ከመሳሰሉት ቅባትነት ካላቸው ምግቦችና ከሚያሰክሩ መጠጦች ራስን መከልከል መከልከል ያስፈልጋል፡፡ (መዝ ፻፰፥፳፬)

ነቢዩ ዳንኤልም በትንቢት መጽሐፉ ስለ መባልዕት ጥሉላት እንዲህ ብሏል‹‹በዚያም ወራት እኔም ዳንኤል ሦስት ሳምንት ሙሉ ሳዝን ነበርሁ፡፡ ማለፊያ እንጀራም አልበላሁም፤ሥጋና የወይን ጠጅም በአፌ አልገባም››(ዳን.፲፥፪-፫) ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ፤‹‹ሌላ ልዩ ትምህርት አታምጡ፤ ልባችሁ በመብል ያይደለ በጸጋ ቢጸና ይበልጣናል፤ በዚያ ይሄዱ የነበሩ እነዚያ አልተጠቀሙምና፡፡›› ለዕብራውያን ሰዎች በጻፈው መልእክቱ ላይ ወንጌል ሥጋን የሚያደልበውን መብልን እንደማትሰብክና በመብል ብቻ ልባችንን ማጽናት እንደሌለብን ገልጿል (ዕብ. ፲፫፥፱)

የክርስትናችን መሠረት ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ስለ መብልና መጠጥ ከንቱነት እንዲህ በማለት አስተምሮናል፡፡ ‹‹ራሳችሁን ጠብቁ፤ በመብልና በመጠጥ፤በመቀማጠልና የዓለምን ኑሮ በማሰብ ልባችሁን አታደንድኑ፤ ያቺ ቀንም በድንገት ትደርስባችኋለች፡፡››(ሉቃ.፳፩፥፴፬)

የሰው ልጅ አብዝቶ በበላና በጠጣ ጊዜ ከአእምሮው በመውጣት እኩይ ተግባራትን ሊፈጽም ይችላል፡፡ ጥጋብና ስካር የኅሊናን አቅል በማሳጣት ለኃጢአት ይዳርጋሉ፡፡ ‹‹በቀን እንደሚሆን በጽድቅ ሥራ እንመላለስ፤በዘፈንና በስካር፤በዝሙትና በመዳራት አይሁን፤በክርክርና በቅናት አይሁን››(ሮሜ ፲፫፥፲፫)  ስካር ከእግዚአብሔር መንግሥት ያርቃል ‹‹ምቀኝነት፤መግደል፤ስካር፤ዘፋኝነት፤ይህንም የሚመስል ነው፡፡አስቀድሜም እንደ ነገርኋችሁ ይህን የሚያደርግ የእግዚአብሔርን መንግሥት አያይም፡፡›› (ገላ.፭፥፳፩) ስካር የሰው አዕምሮን ያጠፋል፡፡(ሆሴ.፬፥፲፩)

ከማንኛውም ክፉ ነገሮች ሁሉ መጠበቅ፤ራስን መግዛት እና መቈጣጠር፤ በንስሓና በጸሎት ወደ እግዚአብሔር መቅረብ፤ እርሱንም ደጅ መጥናትና ለኃጢአታችን ሥርየትን መለምን ማለት ነው፡፡ ይህንንም ስናደርግ ነቢዩ ዳንኤል ‹‹ማቅ ለብሼ በአመድም ላይ ሆኜ ስጾም እጸልይና እለምን ዘንድ ፊቴን ወደ ጌታ ወደ አምላክ አቀናሁ።›› በማለት እንደተናገረው አምላካችን እግዚአብሔር የሚወደውን የተቀደሰውን ጾም በመጾም ለነፍሳችን መልካም ዋጋን እናገኝ ዘንድ ከሥጋዊ ምቾትና ቅንጦት በመራቅና ራሳችንን ዝቅ በማድረግ ልንጾም ይገባል፡፡(ዳን.፱፥፫)

እንግዲህ ጾም ከመንፈሳዊ ተጋድሎ አንዱ ነው፤ ለሥጋም መንፈሳዊ ልጓም ነው፡፡ አንድ ክርስቲያን ፈቃደ ሥጋውን እየገታ ነፍሱን የሚያለመልምበት መንፈሳዊ ስንቅ ነው፡፡ ‹‹ጾም ቊስለ ነፍስን የምትፈውስ፤ኃይለ ፍትወትን የምታደክም፤ የበጎ ምግባራት ሁሉ መጀመሪያ፤ከእግዚአብሔር ጸጋን የምታሰጥ፤የወንጌል ሥራ መጀመሪያ፤የጽሙዳን ክብራቸው፤የደናግል የንጽሕና ጌጣቸው፤ የዕንባ መፍለቂያዋ፤ አርምሞን (ዝምታን) የምታስተምር፤ ለበጎ ሥራ ሁሉ የምታነቃቃ፤ ሰውነትን በእግዚአብሔር ፊት በማዋረድ ትሕትናን ገንዘብ ለማድረግ የምትረዳ መድኃኒተ ነፍስ ናት፡፡››(ማር ይስሐቅ አንቀጽ ፬ ምዕ. ፮)

እግዚአብሔር አምላክ ሰውን በአምሳሉና በአርአያው ከፈጠረው በኋላ ከማእከለ ምድር (ኤልዳ) ወደ ኤዶም ገነት በመውሰድ ክፉውንና መልካሙን የሚለይበት አስተዋይ ኅሊና ባለቤት አድርጎ አኖረው፡፡ (ኩፋሌ ፬፥፱) በዚህም መሠረት የሰው ልጅ ‹‹ከዚህ አትብላ›› በሚል አምላካዊ ቃል ጾም ኆኅተ ጽድቅ የጽድቅ በር ሆና የተሰጠች የመጀመሪያቱ ሕግ ናት፡፡ ጾም ከምግባረ ሃይማኖት ዋነኛው ነው፤ይህም ለአንድ ክርስቲያን በሕይወት ዘመኑ ሁሉ የማይለየው ምግባር ነው፡፡ ጾም የሰው ልጅ ለአምላኩ ለልዑል እግዚአብሔር ያለውን ፍቅር የሚገልጥበት፤መንፈሳዊ ተጋድሎዎችን የሚያከናውንበት፤ስለራሱና ስለወገኖቹ ኃጢአት የሚያዝንበት፤ የሚያለቅስበትና ወደ ንስሓ የሚመለስበት ታላቅ ሥርዓት ነው፡፡

የጾም አስፈላጊነት በክርስትና ሕይወት እጅግ የጎላ ነው፡፡ በመሆኑም በጾም ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ ማስገዛትና ከሥጋዊ ከንቱ ኃጢአት ለመራቅ ይረዳናል፡፡ ሥጋ በምግብ ሲደነድን ለፍትወትና ለተለያዩ ሥጋዊ ኃጢአቶች ቅርብ ይሆናል፡፡ የሥጋ ፍላጎት በቀዘቀዘ ቊጥር ነፍስ ትለመልማለች፤ ለአምላክ ሕግና ትእዛዛት ሁሉ ተገዢ ትሆናለች፡፡ ማኅሌታዊ ቅዱስ ያሬድ  ስለ ጾም እንዲህ ብሏል፤‹‹ጾም ትፌውስ ቊስለ ነፍስ፤ ወታጸምም ኵሎ ፍትወታተ ዘሥጋ ፤ ትሜህሮሙ ጽሙና ለወራዙት፤ ጾም የነፍስን ቊስል ትፈውሳለች፤የሥጋን ፍትወታት ሁሉ ታጠፋለች፤ ለወጣቶችም ትሕትናን ታስተምራለች፡፡››

ለክርስቲያን የነፍስን ሥራ መሥራት  ከእግዚአብሔር ጋር መተባባርና አንድ ወገን እንደመሆን ያለ ምግባር ነው፡፡‹‹አሁንም ወንድሞቻችን በዚህ በሥጋችን ሳለን ፈቃደ ሥጋችንን ልንሠራ አይገባንም፡፡ ፈቃደ ሥጋቸውን የሚሠሩ ሰዎች ሁሉ በወዲሁ አለን ሲሉ በወዲያው ምውታን ናቸውና፡፡ ፈቃደ ሥጋችሁንስ በፈቃደ ነፍሳችሁ ድል ከነሣችሁት ለዘለዓለሙ ሕያዋን ትሆናላችሁ፡፡ ፈቃደ ነፍስን የሚሠሩ ሰዎች ሁሉ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸውና፡፡›› (ሮሜ ፰፥፲፪-፲፬) እንዲል፡፡

ጾም የኃጢአት ሥርየትን ለማግኘትና ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ ይረዳል፡፡ አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ወደ እርሱ በጾምና በጸሎት እንድንመለስ በነቢያት አድሮ አሥተምሮናል፡፡ ‹‹በፍጹም ልባችሁ፤በጾምም፤በልቅሶና በዋይታ ወደ እኔ ተመለሱ፡፡››(ኢዩ.፪፥፲፪)

ጾም በጸጸት መንፈስ ሆነን በንጹሕ ልባችን ወደ ልዑል እግዚአብሔር በንስሓ እንድንመለስ ይረዳናል፡፡ ‹‹ወሀበነ ጾመ ለንስሓ በዘይሰረይ ኃጢአት፤ ኃጢአት የሚሠረይበትን ይቅር የሚባልበትን ጾምን ሰጠን›› ጾም በደልን አምኖና ጥፋትን ተቀብሎ በፍጹም ትሕትና ወደ እግዚአብሔር በመቅረብ በድያለሁ ማረኝ ይቅር በለኝ በማለት የንስሓ ዕንባን በማንባት ከእግዚአብሔር ምሕረትን የምናገኝበት ምግባር ነው፡፡

በመጽሐፍ «የእስራኤልም ልጆች ሁሉ ሕዝቡም ሁሉ ወጥተው ወደ ቤቴል መጡ፤ አለቀሱም፤ በዚያም በእግዚአብሔር ፊት ተቀመጡ፤ በዚያም ቀን እስከ ማታ ድረስ ጾሙ፤ በእግዚአብሔር ፊት የሚቃጠል መሥዋዕትንና የደኅንነት መሥዋዕትን አቀረቡ›› እንደዚሁም ፤«ወደ መሴፋ ተሰበሰቡ፤ ውኃም ቀድተው በእግዚአብሔር ፊት በምድር ላይ አፈሰሱ፤ በዚያም ቀን ጾሙ፤ በዚያም፤ በእግዚአብሔር ፊት በድለናል አሉ፤ሳሙኤልም በእስራኤል ልጆች ላይ በመሴፋ ፈረደ›› (መሳ.፳፥፳፮፤፩ኛሳሙ.፯፥፮)

በቤተክርስቲያናችን ሥርዓተ ጾም መሠረት ጾምን የፈቃድ ጾም (የግል ጾም) እና የዐዋጅ ጾም (የሕግ ጾም) በማለት በሁለት ከፍለን የምንመለከታቸው ሲሆን የግል ጾም የምንለው ምእመናን ለንስሓ በግል የሚጾሙትን የፈቃድ ጾም ነው፡፡ ይህ ጾም ምእመናን በምክረ ካህናት ወይም ከንስሓ አባታቸው ጋር በመመካከርና ቀኖናን በመቀበል የሚጾሙት ጾም ሲሆን አንዱ ሲጾም ሌላው ማወቅ የለበትም፡፡ የዐዋጅ አጽዋማት የምንላቸው ደግሞ ዕድሜያቸው ሰባት ዓመት ከሞላቸው ሕፃናት ጀምሮ መላው ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን በኅብረት በግልጽ የሚጾሟቸው አጽዋማት ናቸው፡፡

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

ዕረፍት ያጣች ነፍስ!

በሕይወት ሳልለው

እግዚአብሔር አምላካችን በአርአያውና በአምሳሉ ሲፈጥረን በክብር ነውና ከአለመኖር ወደ መኖር ያመጣንም በእስትንፋሱ ነበር፡፡ «እግዚአብሔር አምላክም ሰውን ከምድር አፈር ፈጠረው፤ በአፍንጫውም የሕይወት እስትንፋስን እፍ አለበት፤ሰውም ሕያው ነፍስ ያለው ሆነ»፤ (ዘፍ ፪፥፯)፤

አባታችን አዳም ባደረገው ስሕተት ከገነት ተባሮ ወደ ምድር ከወረደ በኋላ ኑሮው የከፋ ነበር፤ ብዙም ተፈትኗል፤ ገነት ሳለ ደስታን እንጂ መከራን አላወቀም፤ ነገር ግን እዚህ ምድር ላይ በፍርሃትና በጭንቀት ይኖር ነበር፡፡ ከልብሰ ብርሃንም ተራቆተ፤ ተበረደ፤ የበለስ ቅጠል ቆርጦም ለበሰ፤ በመከራውም ጊዜ የፈጣሪውን ትእዛዝ በመተላለፉ የሠራውን ኃጢአቱን በማሰብ ያለማቋረጥ ያለቅስ ነበር፡፡ ከብዙ ዘመናት በኋላም በተገባለት ቃልኪዳን መሠረት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከልጅ ልጁ ተወልዶ እስኪያድነው ድረስ በምድር ብዙ ተሠቃይቷል፡፡

ሰው ድኅነትን የሚያገኘው በክርስትና ሕይወቱ ውስጥ ለእምነትና ለሃይማኖቱ መሥዋዕትነት በመክፈል፤ ዘወትር በክርስቲያናዊ ሥርዓት፤ በምስጋናና በሕገ እግዚአብሔር ሲኖር ነው፡፡ ነገር ግን ዓለማችን በአሁኑ ጊዜ በኃጢአት ማዕበል ውስጥ ተዘፍቃለች፤ መከራ፤ ሥቃይ፤ ችግር፤ እንዲሁም ጦርነት በየሀገሩ በዝቷል፡፡ ትንቢቱም እንደሚገልጸው «ሕዝብ በሕዝብ ላይ፤ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣሉ፤ በየሀገሩም ረኃብ፤ ቸነፈርም፤ የምድር መናወጥም ይሆናል፤ እነዚህም ሁሉ የምጥ ጣር መጀመሪያ ናቸው፡፡ ያንጊዜም ለመከራ አሳልፈው ይሰጡአችኋል፤ ይገድሉአችኋልም፤ ስለ ስሜም በሰዎች ሁሉ ዘንድ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ፡፡ ያን ጊዜም ብዙዎች ሃይማኖታቸውን ይለውጣሉ፤ እርስ በእርሳቸውም አሳልፈው ይሰጣጣሉ፤ እርስ በእርሳቸውም ይጣላሉ» (ማቴ. ፳፬፥፯-፲)፡፡

በዚህች ምድር ላይ ስንኖር ልንፈተን እንችላለን፤ በዕለት ክንዋኔያችን ውስጥ ብዙ ውጣ ውረድ ሊገጥመን ይችላል፡፡ ከጥንት ጀምሮ አእምሮአችንን ለመቆጣጠርና ትዕግስትን አስጨርሶ ተስፋ ለማስቆረጥ የሚፈታተነን ጠላት ዲያብሎስ የማሳቻ መንገዱ ብዙ ነውና በእምነት ጸንተን ልንኖር ይገባል፡፡ ተስፋ የቆረጠ ሰው ለውድቀትና ለጥፋት የቀረበ ይሆናል፤ ዕረፍትን የሚሻ ሰው ግን በተስፋ ውስጥ ለእያንዳንዱ ችግር መፍትሔ እንዳለው፤ ለእያንዳንዱ ለተቆለፈ መዝጊያ አንድ ወይም ብዙ ቁልፎች እንዳሉትና ለእያንዳንዱ ውድቀትም መነሻ እንዳለው ይታወቃል::

ሰላምና ፍቅር ከእኛ ሲርቅ ማንነታችንን መጥላት፤ የእኛ ያልሆነውን ባዕድ ጠባይ መቀበል እንጀምራለን፤ ነፍስ ግን ሁሌም ፈጣሪዋን ትፈልጋለች፤ እናም ትጨነቃለች፡፡

ዛሬም ያለው ትውልድ ከነፍሱ ይልቅ ለምድራዊ ሕይወቱ ይለፋል፤ ነገር ግን ከንቱ ልፋት ነው፡፡ «ከፀሐይ በታች የተሠራውን ሥራ ሁሉ አየሁ፤ እነሆም፥ ሁሉ ከንቱ ነው፥ነፋስንም እንደመከተል ነው»መጽሐፈ መክብብ ፩፥፲፬፡፡የሰው ልጅ ኅሊናውን ሳይክድ ለእምነቱ ተገዝቶ ሲኖር ወደ ፈጣሪው መቅረብ ይቻለዋል፤ ሁል ጊዜም አምላኩን ሲያስብ፤ በተስፋም ሲኖር፤ ወደ ክብር ቦታው እንደሚመለስ በማመን በጎ ሥራን አዘውትሮ ይተገብራል፡፡ ፈሪሀ እግዚአብሔር ያለው ሰው ፈጣሪውን ያስባል፤ ይፈራል፤ ያከብራል እንዲሁም በሕጉ ይመራል፤ ከራሱም አልፎ ለሌሎች ጥሩ ማድረግን ይመኛል፤ ያደርጋልም፡፡

እርግጥ ነው ጠባያችን እንደመልካችን ይለያያል፤ እግዚአብሔር አምላካችን በቃሉ «ብዙ ተባዙ፤ ምድርንም ሙሉአት» እንዳለው (ዘፍ. ፩፥፮)፤ በዓለማችን በቢሊዮን የምንቆጠር ሰዎች አለን፡፡ እናም ተከባብሮ የመኖር ውዴታና ግዴታ የእኛ ቢሆንም ኃላፊነትን ከመወጣት ይልቅ ክፋት፤ ተንኮል፤ በደል፤ ጥላቻ፤ ግድያ ከዛም አልፎ  ባዕድ አምላኪም በዝቷል፡፡ ፈውስና በረከት ማጣት፤ በምሬትና በሰቆቃ ውስጥ ለመኖር መንስኤው የኃጢአት መብዛት ነው፤ ክፉውም ሆነ ደጉ የሥራችን ውጤት ነው፡፡

በዚህ ምድር ስንኖር ሥጋችንንም ዋጋ በማሳጣት ለነፍሳችን ልንኖርላት እንደሚገባ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወንጌል አስተምሮናል፤ «ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢገዛ፤ ነፍሱንም ቢያጣ፤ ለሰው ምን ይረባዋል? ሰውስ ለነፍሱ ቤዛ ምን በሰጠ ነበር?» (ማቴ. ፲፮፥፳፮)፡፡

ሰላም ፍቅር ማጣት

የባዶነት ስሜት

ማንነትን መጥላት

በምሬት አንደበት

ክፉ ነገር ማውጣት

ርኩሰት በኃጢአት

ነፃነትን መሻት

  ነፍስ ስታጣ ዕረፍት

የተጨነቀች ዕለት

«እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ ወደ እኔ ኑ፤ እኔም አሳርፋችኋለሁ፤» (ማቴ.፲፩፥፳፰) ይለናልና ፈጣሪያችንን አብዝተን እንለምነው፤ እንጸልይ እንጹም፤ ዕረፍት ያጣች ነፍሳችንን እናሳርፋት፡፡

መንፈስ ቅዱስ

መምህር ቢትወደድ ወርቁ

መንፈስ ቅዱስ ማን ነው? ለሚለው ጥያቄ ብዙዎች የተለያየ ግንዛቤ አላቸው፡፡ አንዳንድ ሰዎች እንደ ረቂቅ ኃይል ይመለከቱታል፡፡ ሌሎች ደግሞ  እግዚአብሔር ክርስቶስ ለደቀመዛሙርቱ የገለጠውና ማንነት የሌለው ኃይል እንደሆነ ይረዳሉ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ግን መንፈስ ቅዱስ እግዚአብሔር እንደሆነ ያውጃል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም  አእምሮ ያለው ማንነት፤ ስሜትና ፈቃድ ያለው መለኮታዊ አካል እንደሆነ ይነግረናል፡፡ ቅዱስ ባስልዮስ «እኔ እግዚአብሔር በምልበት ጊዜ አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ማለቴ ነው» ብሎ እንደተናገረው እግዚአብሔር የሚለው ስም የሥላሴ መጠሪያ ነው፡፡ የአብ የወልድ እስትንፋሳቸው የሆነ መንፈስ ቅዱስም ከአብ ከወልድ ጋር በዕሪና በፍጹም መተካከል ያለ ነውና እግዚአብሔር መሆኑን እንመሠክራለን፡፡ ይኽውም የቅዱሳን ነቢያት ሐዋርያትና መምህራን ትምህርት ምስክር ነው፡፡

ነቢዩ ኢሳይያስ ንጉሡ በራእዩ ዖዝያን በሞተበት ዓመት እግዚአብሔርን በረጅምና ከፍ ባለ ዙፋን ላይ ተቀምጦ እንዳየው፤ ሱራፌልም በሁለት ክንፎቻቸው ፊታቸውን፤ በሁለት ክንፎቻቸው እግሮቻቸውን እየሸፈኑ፤ በሁለት ክንፎቻቸውም ከጽንፍ ጽንፍ እየበረሩና አንዱም ለአንዱ «ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ፤ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር፤ ምድር ሁሉ በቸርነትህ ተሞልታለች» እያሉ እንደሚያመሰግኑት ነግሮናል፡፡ ሊቃውንቱ ሱራፌል ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ብለው ያመሰገኑበትን ምሥጢር ሲያብራሩ፤ ቅዱስ የሚለው ቃል አለመለወጡ፤ ሦስቱ አካላት በባሕርይ፤ በህልውና፤ በሥልጣን፤ በአገዛዝና በመሳሰለው አንድ መሆናቸው ሳይለወጥ ሦስት መሆኑ የእግዚአብሔርን የአካል ሦስትነት የሚገልጥ መሆኑን ያስረዳሉ፡፡(ኢሳ.፮፥፩-፱) ይህ የሊቃውንቱ ትምህርት እውነተኛ መሆኑ ማስረጃው ነቢዩ ኢሳይያስ በመንፈስ ቅዱስ መነጽር እንደተመለከተው በሐዲስ ኪዳንም የራእይ አባት (አቡቀለምሲስ) የተባለው ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስም በእግዚአብሔር ዙፋን መካከል ያሉ የሰው፤ የአንበሳ፤ የላምና የንሥርን ፊት ይመስላሉ፡፡ እነርሱም ኪሩቤል ቃሉ ሳይለወጥ «ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ፤ የነበረና ያለ፤ የሚመጣውም፤ ሁሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክ» እያሉ ቀንና ሌሊት ያለ ዕረፍት እንደሚያመሰግኑ መናገሩ ነው፡፡ (ራእ.፬፥፰)

ዳግመኛም ነቢዩ ኢሳይያስ በምዕራፍ ፮ ቁጥር ፱ ላይ «የጌታንም ድምጽ ማንን እልካለሁ? ማንስ ይሄድልናል?» ሲል ሰማሁ ይላል፡፡ ተናጋሪው ጌታ እግዚአብሔር ማንን እልካለሁ? ማለቱ ባሕርያዊ አንድነቱን ማንስ ይሄድልናል? ብሎም ሦስትነቱን ገልጧል፡፡ ነቢዩ ማንን እልካለሁ? ማንስ ይሄድልናል? ብሎ እግዚአብሔር ለተናገረው ነገር ‹‹እኔን ላከኝ›› ካለው በኋላ በረጅምና ከፍ ባለ ዙፋን ተቀምጦ የተገለጠለት እግዚአብሔር ‹‹ሂድና ይህን ሕዝብ መስማትን ትሰማላችሁ አታስተውሉም፤ ማየትንም ታያላችሁ አትመለከቱም፤ በላቸው አለኝ›› በማለት ተናገረ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በወንጌሉና ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ መንፈስ ቅዱስ እግዚአብሔር መሆኑን በግልጥ መስክረዋል፡፡(ዮሐ.፲፪፥፴፱-፵፩፤የሐዋ.፳፰፥፳፭-፳፯) ቅዱስ ጳውሎስ በዚህ ኃይለ ቃል ብቻ ሳይሆን በኦሪት፤ በነቢያት፤ በጸጋና በረድኤት አድሮባቸው ሕዝቡን ሲመክር፤ሲያስተምርና ሲገሥጽ የነበረ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ መሆኑን ደጋግሞ አስተምሯል፡፡ ይኽው ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ በፍጹም የማይመረመር፤ የማይታወቅ፤ የእግዚአብሔር ጥልቅ ባሕርይ የሚታወቀው፤ በራሱ በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ብቻ እንደሆነ የመንፈስ ቅዱስን ነገር በስፋት እንዳስተማረ እንረዳለን፡፡(፩ቆሮ.፪፥፲፩፤ዕብ.፫፥፯)

መንፈስ ቅዱስ እግዚአብሔር የመሆኑ እውነታ  በብዙ ቅዱሳት መጽሐፍት ውስጥ በግልጽ ተነግሮአል፡፡ቅዱስ ጴጥሮስ ሐናንያ ለምን እንደዋሸ ሲጠይቀው  ‹‹ሐናንያ ሆይ መንፈስ ቅዱስን ታታልልና ከመሬቱ ሽያጭ ታስቀር ዘንድ ሰይጣን ስለምን በልብህ ሞላ? ሳትሸጠው የአንተ አልነበረምን? ከሸጥከውስ በኋላ በሥልጣንህ አልነበረምን? ይህንን ነገር በልብህ ስለምን አሰብህ? እግዚአብሔርን እንጂ ሰውን አልዋሸህም አለው›› ይለናል፡፡ እንግዲህ ከዚህ ኃይለ ቃል ሐናንያ እግዚአብሔርን እንጂ ሰውን እንዳልዋሸ፤ ይህ ደግሞ መንፈስ ቅዱስ እግዚአብሔር እንደሆነ በግልጽ እንረዳለን(የሐዋ.ሥራ ፭፥፫-፬)፡፡

ከዚህ በተጨማሪም ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ «አቤቱ  ከመንፈስህ ወዴት እሄዳለሁ? ከፊትህስ ወዴት እሸሻለሁ? ወደ ሰማይ ብወጣ፤ አንተ በዚያ አለህ፤ ወደ ሲኦልም ብወርድ፤ በዚያ አለህ።» በማለት ተናግሯል፡፡ ይህ ደግሞ በሰማይ በምድርም፤ በጠፈርም በጥልቁም ምሉዕ ሆኖ መገኘት የእግዚአብሔር መለኮታዊ ባሕርዩ ስለሆነ መንፈስ ቅዱስ በሁሉም ሥፍራ የሚገኝ ፍጹም ምሉዕ አምላክ መሆኑን ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ ይነግረናል (መዝ. ፻፴፱፥፯-፰)፡፡ መንፈስ ቅዱስ በእርግጥ መለኮታዊ ማንነት እንደሆነ ማወቅ እንችላለን፤ ምክንያቱም አዕምሮ፤ ስሜቶችና ፈቃድ አለው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ያስባል፤ያውቃልም (፩ኛ ቆሮ. ፪፥፲)፡፡ መንፈስ ቅዱስ ሊያዝን ይችላል፡፡  (ኤፌ. ፬፥፴) መንፈስ ለእኛ ይማልድልናል (ሮሜ ፰፥፳፮-፳፯)፡፡ እንደ ፈቃዱ ውሳኔዎችን ያደርጋል፡፡ (፩ኛ ቆሮ.፲፪፥፯-፲፩) መንፈስ ቅዱስ እግዚአብሔር ነው፡፡

ጻድቁ ኢዮብም በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ‹‹የእግዚአብሔር መንፈስ ፈጠረኝ፤ ሁሉን የሚችል የአምላክ እስትንፋስ ሕይወትን ሰጠኝ›› እንደዚሁም ‹‹በመንፈሱ ሰማያት ውበትን አገኙ›› በማለት ደጋግሞ መናገሩ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ፈጣሪ መሆኑን ያስረዳል፡፡እነዚህ ኃይለ ቃላት የሚያስረዱን መንፈስ ቅዱስ ፈጣሪ፤ ሁሉን ቻይና የአምላክ (የአብ የወልድ) እስትንፋሳቸው መሆኑን ነው፡፡

እግዚአብሔር አካላዊም ነው፡፡ ነገር ግን እንደፍጡራን አካል በሰው ልጅ ልቡና የሚመረመር  አይደለም፡፡ (ኢዮ.፲፩፥፯፤፩ቆሮ.፪፥፲-፲፭፤ሮሜ ፲፩፥፴፫) ወንጌላዊው ዮሐንስም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር አካል ረቂቅ መሆኑን ሲያስተምር «እግዚአብሔር መንፈስ ነው» ብሎናል፡፡ (ዮሐ. ፬፥፳፬) እግዚአብሔር መንፈስ መባሉም አካል የሌለው ማለት ሳይሆን አካሉ የማይመረመር የማይዳሰስ የማይጨበጥ የማይታይ መሆኑን ለመገለጽ ሲሆን መንፈስ ቅዱስም መንፈስ መባሉም አካላዊና አካሉም ረቂቅ መሆኑን ለመግለጥ ነው፡፡ ክብር ይግባውና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ቃለ ሰብእ እንደ ቃለ መላእክት ዝርው ያይደለ፤ የአብ የመንፈስ ቅዱስ አካላዊ ቃል እንደሚባል ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ በወንጌሉ አስቀድሞ ነግሮናል፡፡ (ዮሐ.፩፥፩-፫) ስለዚህም ሁሉን የሚችል የአምላክ እስትንፋስ የተባለ መንፈስ ቅዱስ የአብ የወልድ አካላዊ እስትንፋሳቻው ነው፡፡ አካላዊ በመሆኑም ከአብና ከወልድ ጋር በክብር ዙፋኑ ላይ ተቀምጦ ለነቢዩ ኢሳይያስ ተገልጧል፡፡(ኢሳ.፮፥፩-፱፤የሐዋ. ፳፰፥፳)

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ለመንፈስ ልጁ ለጢሞቴዎስ በላከው መልእክቱ መንፈስ ቅዱስ አካላዊ በመሆኑ የአካል ክፍል በሆነው አንደበቱ እየተናገረ እንዲህ ሲል መስክሯል ‹‹መንፈስ ግን በግልጥ በኋለኞቹ ዘመናት አንዳንዶች የሚያስቱ መናፍስትንና በውሸተኞች ግብዝነት የተሰጠውን የአጋንንት ትምህርት እያደመጡ ሃይማኖትን ይክዳሉ ይላል (ይናገራል)››፡፡ (፩ጢሞ.፬፥፩) መንፈስ ቅዱስ መምከር ብቻ ሳይሆን ለሐዋርያትም ስለ አገልግሎታቸው መመሪያን ይሰጣቸው እንደነበርም ‹‹እነዚህም ጌታን ሲያመልኩና ሲጦሙ መንፈስ ቅዱስ በርናባስንና ሳውልን ለጠራኋቸው ሥራ ለዩልኝ አለ›› በማለት ቅዱሳት መጻሕፍት ስለ መንፈስ ቅዱስ አካላዊነት ይናገራሉ፡፡ (የሐዋ.፲፫፥፪) በሰማይ ድል ስለነሱ ቅዱሳን‹‹ከእንግዲህ ወዲህ ለጌታ የሚሞቱ ብፁዓን ናቸው›› ተብሎ በተነገረ ጊዜም እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ የእኛን አካል የፈጠረ አካላዊ ነውና ‹‹አዎን ከድካማቸው ያርፉ ዘንድ ሥራቸውም ይከተላቸዋል›› ብሎ እንደነገረው ባለራእዩ ቅዱስ ዮሐንስ  አስቀድሞ ነግሮናል፡፡ (ራእ.፲፬፥፲፫) ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ከዕርገቱ በኋላ መንፈስ ቅዱስ ወደ እነርሱ እንደሚመጣና ሁሉን እንደሚያስተምራቸው፤ምሥጢራትንም እንደሚገልጥላቸው፤ተአምራት የሚያደርጉበትን ጸጋና ሥልጣንም እንደሚሰጣቸውና መከራን ሁሉ እንዲችሉ ኃይልን እንደሚያስታጥቃቸው በሚገባ አስተምሯቸዋል፡፡ (ዮሐ.፲፬፥፳፮)

አካላዊ ቃል ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ክብር ይግባውና መንፈስ ቅዱስ የሚሠርጸው ከአብ ብቻ እንደሆነ ‹‹ዳሩ ግን እኔ ከአብ ዘንድ የምልክላችሁ አጽናኝ እርሱም ከአብ የሚወጣ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ እርሱ ስለእኔ ይመሰክራል›› በማለት ለቅዱሳን ሐዋርያት አስቀድሞ ነግሮአቸዋል፡፡ (ዮሐ.፲፭፥፳፮) መንፈስ ቅዱስ ከአብ ጋር ወልድን ለድኅነተ ዓለም እንደላከም ተብሎ ተጽፏል ‹‹አሁንም ጌታ እግዚአብሔርና መንፈሱ ልከውኛል›› እንዳለ ፊተኛና ኋለኛ አልፋና ዖሜጋ፤ መጀመሪያውና መጨረሻው የሆነ እግዚአብሔር ወልድም ከዕርገቱ በኋላ በደልን ለማንጻት ምሥጢራትን ለመግለጽ በመንፈሳዊ ሐሴት ኃጢአትን ለማስተሥረይ ከአብ ጋር ሆኖ የባሕርይ ሕይወቱ የሆነ መንፈስ ቅዱስን ልኮታል፡፡ (ኢሳ.፵፰፥፲፪-፲፮፤ራእ.፩፥፰፤፳፪፥፲፫) ሃይማኖታቸው የቀናች ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ ሊቃውንትም በጉባዔ ኒቅያ መቶ ሃምሳው ሊቃውንት በጉባኤ ቁስጥንጥንያ ጌታችን በወንጌል ያስተማረውን ትምህርት መሠረት አድርገው በጸሎተ ሃይማኖት ‹‹ወነአምን በመንፈስ ቅዱስ ዘሠረጸ እም አብ ንስግድ ሎቱ ወንሰብሖ ምስለ አብ ወወልድ ዘነበበ በነቢያት፤በመንፈስ ቅዱስ እናምናለን እርሱም ጌታ ሕይወትን የሚሰጥ ከአብ የሠረጸ ከአብና ከወልድ ጋር በአንድነት እንሰግድለታለን እናመሰግነዋለን፤ እርሱም በነቢያት አድሮ የተናገረ ነው›› ብለው አውጀዋል፡፡

እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ባለበት ሥፍራ ሁሉ አርነት አለ፡፡‹‹የጌታ መንፈስ ባለበት በዚያ አርነት አለ›› ተብሎ እንደተጻፈ፤ አርነቱም ከዲያብሎስ አገዛዝ፤ ከሰይጣናዊ አሠራር፤ ከኃጢአትና ከሥጋ ፈቃድ ሁሉ ነው፡፡ (፪ቆሮ. ፫፥፲፯፤ገላ. ፭፤፲፱) ቅዱሳን ሐዋርያት የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ በወረደላቸው ጊዜ አልጮኹም፤ ተንቀጥቅጠው አልወደቁም፤ የነበሩበትን አካባቢ በጩኽት አላወኩም፤ የእግዚአብሔር የሆኑትን አልተሳደቡም፡፡ የተገለጠላቸውና የተናገሯቸው ቋንቋዎችም፤ በወቅቱ ከመላው ዓለም የመጡ ሰዎች ይናገሩባቸው የነበሩ ቋንቋዎች (ልሳናት) ናቸው፡፡ቅዱሳን ሐዋርያት ከመንፈስ ቅዱስ በተገለጠላቸው የተለያዩ ቋንቋዎች ዓለም ክርስቶስን በማመን፤ ጽድቅን በመከተል፤ የሰውን ዘር በሙሉ እንደራሱ እንዲወድ፤ ለኔ የሚያስፈልገኝ ለሌላውም ያስፈልገዋል እንዲል አስተማሩት፡፡መንፈስ ቅዱስ ባለበት ሥፍራ ከልዩነት አንድነት፤ ከእኔነት ይልቅ ለእኛ ማለት፤ ከመገፋፋት መደጋገፍ፤ ከመበታተን መሰባሰብ፤ ከትዕቢትና ከዕብሪት ትሕትና ጎልቶ ይታያል፡፡ስለዚህም በቅዱሳት መጻሕፍት ‹‹መንገዳችንን እንመርምርና እንፈትን›› እንደዚሁም ደግሞ ‹‹በሃይማኖት ብትኖሩ ራሳችሁን መርምሩ›› ተብሎ እንደተነገረ፤ የምንጓዝበትን መንገድና አስተሳሰባችንን ከዚህ አንጻር ልንመረምር ይገባናል፡፡ (ሰቆ.ኤር. ፫፥፵፤፪ቆሮ.፲፫፥፭)

የጸጋ ሁሉ ባለቤት፤ ፈጣሪ ፍጡራን፤ አምጻኤ ዓለማት፤ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በቸርነቱ ለክብርና ለመንግሥተ ሰማያት ያብቃን፤ አሜን!!!

አንቲ ውእቱ ጽጌ መዓዛ ሠናይ (ውዳሴ ማርያም ዘእሑድ)

                                                                                መ/ር ዘለዓለም ሐዲስ
ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፭ ያለው ዘመን ወርኀ ጽጌ በመባል ይታወቃል፡፡ወርኀ ጽጌም የተባለበት ምክንያት ዕፀዋቱ አብበው ምድርን በአበባነታቸው አሸብርቀው የሚታዩበት ወር በመሆኑ ነው፡፡ጽጌ ማለት ጸገየ አበበ ካለው የግእዝ ሐረግ የተመዘዘ ሲሆን ጽጌ ትርጉሙ አበባ ማለት ነው ጌታችን በጽጌ መስለው የተናገሩ ነቢያት ናቸው ከዐበይት ነቢያት አንዱ የሆነው ኢሳይያስ ጌታን ከዕሤይ ሥር በትር ትወጣለች ከርሷም አበባ ይገኛል በማለት ጌታን በአበባው እመቤታችን በበትር መስሎ ተናግሯል፡ንጉሥ ሰሎሞንም በመኃልዩ“ጽጌ አስተርአየ በውስተ ምድርነ በምድራችን አበባ ታየ”በማለት ጌታን በአበባ እመቤታችን በምድር ይመስላታል(ኢሳ ፲፩፥፩)

የዘመነ ሐዲስ ሊቃውንትም የነቢያትን ምሳሌያዊ ምስጢር ከማብራራታቸው በተጨማሪ እመቤታችን በጽጌ በአበባ፣ልጇን ከአበባው በሚገኘው ፍሬና መዓዛ መስለው ተናግረዋል ከእነዚህ ሊቃውንት መካከል አንዱ የሆነው ቅዱስ ኤፍሬም “አንቲ ውእቱ ጽጌ መዐዛ ሠናይ እንተ ሠረጸት እምሥርወ ዕሤይ ከዕሤይ ሥር የተገኘች መዓዛዋ ያማረ ጽጌ አንቺ ነሽ በማለት እመቤታችን በአበባ (በጽጌ) ልጇን በመዓዛው መስሎ ተናግሯል ሌሎችም ሊቃውንት ተመሳሳይ ምሳሌ በመመሰል ምስጢረ ሥጋዌውን አብራርተዋል፡፡

ይህ ወራት በቀደሙት አባቶቻችን ዘንድ እስከ ፲፫ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ዘመነ ጽጌ እየተባለ እግዚአብሔር ምድርን በአበባ ማስዋቡ በቤተ ክርስቲያን ቢዘከርም እንደ አሁኑ ማኅሌተ ጽጌ ሰቆቃወ ድንግል እየተቆመ የእመቤታችን ስደት አይታሰብበትም ነበር፡፡ወቅቱ እግዚአብሔር ምድርን በአበባዎች የሚያስጌጥበት ስለሆነ ቅዱስ ያሬድ በዚህ ወቅት ምድር በአበባ የሚያስውቡትን የሽቱ ዕፀው ናርዶስ ቀንሞስ ሮማን የመሳሰሉትን እያነሣ ምድር በእነዚህ ሁሉ አበባዎች እንዳጌጠችና እንደተዋበች የተናገረውን የየየቀኑን መዝሙር እየዘመረች ቤተ ክርስቲያናችን እግዚአብሔርን ታመሰግንበት ነበር፡፡በኋላ ግን ከቅዱስ ያሬድ ቀጥለው የተነሱት ሊቃውንት ስለእመቤታችን መሰደድ ድርሰት የደረሱ ሊቃውንት የነቢያትን ምሳሌ መነሻ በማድረግ እመቤታችን አበባውን በሚያስገኙ ያማሩ ያማሩ የሽቱ ዕፀው፣ልጇን በጽጌ በአበባ እየመሰሉ ማኅሌተ ጽጌና ሰቆቃወ ድንግልን ከደረሱ ማኅሌቷንም መቆም ከጀመሩ በኋላ ወርኃ ጽጌ ተብሎ ከመታሰቡ በተጨማሪ የእመቤታችን የስደቷ መታሰቢያ ሁኖ መከበር ጀምሯል፡፡

በ፲፫ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በአባ ዜና ማርቆስ አስተማሪነት ከአይሁዳዊነት ወደ ክርስቲያንነት የተመለሰው አባ ጽጌ ብርሃንና (ጽጌ ድንግል) አባ ገብረ ማርያም መምህር ዘደብረ ሐንታው ሁለቱ ማኅሌተ ጽጌንና ሰቆቃወ ድንግልን ደርሰው የእመቤታችን ስደት እያሰቡ ማኅሌት መቆም ከጀመሩበት ከ፲፫ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ ማኅሌቱ ሳይቋረጥ ቀጥሏል፡፡ምእመናንንም የእመቤታችን ስደት ለማስታወስ በእመቤታችን ስም ማኅበር እየጠጡ ምንም ጾሙ የፈቃድ ቢሆንም ጾም እየጾሙ ዝክር እየዘከሩ ያከብሩታል ማኅበሩም የሚጠጣው በቤተ ክርስቲያን ወይም በተራራ ላይ ነው ከቤታቸው የማይጠጡበት ምክንያት እመቤታችን በረሃ ለበረሃ ስለተሰደደች ያንን ለማስታወስና እንደ እመቤታችን በመንገድ የደከመን እንግዳ ለመቀበል ነው፡፡
የማኅሌተ ጽጌ ደራሲ የሆነው አባ ጽጌ ብርሃን (ድንግል) ከመጠመቁ በፊት ዘካርያስ ተብሎ ይጠራ ነበር ለማመን ያበቃችውም ገባሪተ ኃይል የሆነች የእመቤታችን ሥዕል ናት ብዙ ተአምራትን ስታደርግ ስላየ ወደአባ ዜና ማርቆስ በመሔድ ተምሮ ለማመን በቅቷል ከአባ ዜና ማርቆስ ትምህርተ ሃይማኖትን ተምሮ በምንኵስና ሕይወት መኖር ከጀመረ በኋላም ያችን ለማመን ያበቃችውን ገባሪተ ኃይል ሥዕል ሳይሳለም አይውልም ነበር፡፡

ከሥዕሏ ፊትም ሲቆም የሚያቀርበው እጅ መንሻ (መባዕ) ስለሌው ይጨነቅ ነበር በኋላ ግን ይህ ዘመነ ጽጌ ሲደርስ በየቀኑ ሃምሳ ሃምሳ የጽጌረዳ አበባ እየፈለገ እንደ ዘውድ እየጎነጎነ ለዚያች ምስለ ፍቁር ወልዳ ሥዕል ያቀዳጃት ነበር በጋው ሲወጣ የጽጌረዳው አበባ ስለደረቀበት ከሥዕሏ ተንበርክኮ እመቤቴ በየቀኑ የማመጣልሽ የጽጌረዳ አበባ ደረቀ ስለአበባው ፈንታ መልአኩ ተፈሥሒ ተፈሥሒ እያለ ያመሰገነሽን ምስጋና በአበባው ቁጥር ልክ ሃምሳ ሃምሳ ጊዜ እንዳመሰግንሽ ፍቀጅልኝ በማለት ተማጸነ ከዚህ በኋላ በየቀኑ ተፈሥሒ ፍሥሕት የሚለውን የመልአኩን ምስጋና በየቀኑ ሲያቀርብላት ምስጋናው እንደጽጌረዳ አበባ እየሆነ ከአንደበቱ ሲወጣ እመቤታችን አበባውን እየተቀበለች ስትታቀፈው ሰዎች እያዩ ያደንቁ እንደነበር ገድለ ዜና ማርቆስ ያስረዳል፡፡
እሱም በድርሰቱ እንዲህ ሲል ገልጾታል“አባዕኩ ለኪ ስብሐተ ተአምር ዘይሤለስ በበሃምሳ ህየንተ ጽጌያት ሃምሳ ለስዕልኪ አክሊለ ርእሳ” ለስዕልሽ ዘውድ ይሆን ዘንድ ሃምሳ የጽጌ ረዳ አበባ አቀርብልሽ ስለነበረው ፈንታ ሦስት ጊዜ ሃምሳ(መቶሃምሳ) የሚሆን ምስጋናን አቀረብኩልሽ በማለት፡፡ስለዚህ ዘመነ ጽጌ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ እግዚአብሔር ምድርን በአበባ ማስጌጡን ማሰባችን እንዳለ ሁኖ በተጨማሪ የእመቤታችን የስደቷን በዓል እናስብበታለን፡፡

                                           ስለምን ወደግብፅ ተሰደደ?   

ጌታችን ከመወለዱ በፊት ከጽንሰቱ እስከ ዳግም ምጽአቱ ድረስ ስለሚሠራው ሥራ አስቀድሞ በነቢያቱ እያደረ ትንቢት አናግሯል፡፡ መልአኩም ለዮሴፍ ብላቴናውን ሄሮድስ እንደሚገድለው ሲነግረው የሚሸሽበትን ቦታ ሳይቀር “ተንሥእ ንሣእ ሕፃነ ወእሞ ወሑር ውስተ ብሔረ ግብፅ” ተነስተህ እናቱንና ብላቴናውን ይዘህ ወደግብፅ ሽሽ በማለት ለስደቱ ግብፅን እንደመረጣት በትንቢቱ ተናግሯል(ማቴ፪፥፲፫) ከደቂቅ ነቢያት አንዱ ሆሤዕም ጌታችን ወደግብፅ እንደሚሰደድ “እምግብፅ ጸዋእክዎ ለወልድየ ልጄን ወደግብፅ ጠራሁት” ሲል ልዑለ ቃል ኢሳይያስ ደግሞ “ወይወርድ እግዚእነ ውስተ ምድረ ግብፅ እንዘ ይጼዐን ዲበ ደመና ቀሊል፤ጌታችን በፈጣን ደመና (በእመቤታችን ጀርባ) ተጭኖ ወደግብፅ ይወርዳል በማለት ተናግሯል (ሆሴ፲፩፥፩ ኢሳ ፲፱፥፩)ከሌሎች ሀገሮች ለስደቱ ግብፅ የተመረጠችበት ምክንያቱ ብዙ ቢሆንም ጥቂቶቹን እንመለከታለን፡፡
፩.ለፍቅሩ ስለሚሳሱለት፤ ጌታችን ወደግብፅ የተሰደደበት ምክንያት ግብፃውያን ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ ጌታችን ከምንም በላይ ለፍቅሩ ይሳሱለት ስለነበረ ነው፡፡ይህንም ወደ ግብፅና ወደ ኢትዮጵያ በተሰደደ ጊዜ ግብፃውያንና ኢትዮጵያውያን እንዴት አክብረው እንደተቀበሉትና እንደሳሱለት በነገረ ማርያም የተጻፈው ታረክ ጥሩ ማስረጃ ነው ምንም ሰይጣን ያደረባቸው እነ ኮቴባን የመሰሉ አንዳንድ ክፉ ሰዎች ቢያጋጥሟቸውም ብዙዎቹ ደግሞ ለፍቅሩ በመሳሳት“ደም ግባቱ ከሰው ልጆች ሁሉ ያምራል”ተብሎ የተነገረለትን መልኩን በማየት ብቻ ለማመን የበቁ ደጋጎች ነበሩ እንኳን ቤት መስርተው በዓለም የሚኖሩት በበረሃ ውስጥ የሚኖሩ ሽፍታዎችም ለጌታችን ያሳዩት ርኅራኄና ፍቅር የተለየ ነበር፡፡ሕፃኑ ኢየሱስ ክርስቶስና እመቤታችን ዮሴፍና ሰሎሜ ኢየሩሳሌምን ለቀው ወደ ግብፅ ሲሰደዱ ግብፃዊው ጥጦስና አይሁዳዊ ዳክርስ ሁለት ወንበዴዎች በረሃ ውስጥ አግኝተዋቸው ነበር እስራኤላዊዉ ዳክርስ ልብሳቸውን ለመግፈፍ ሲፋጠን ግብፃዊዉ ጥጦስ ግን በልቡናው ርኅራኄ አድሮበት ለፍቅሩ በመሳሳት እነዚህ ሰዎች የቤተ መንግሥት ሰዎች ናቸው አሳዘኑኝ ወደ ዚህ ቦታ የመጡት ያለ ምክንያት አይሆንምና አንቀማቸው እንተውላቸው በማለት ለጌታ ያለውን ፍቅርና ርኅራኄ ገልጧል
ወደ ኢትዮጵያም በመጡበት ወራት ቤታቸውን እየለቀቁ ያስተናግዷቸው እንደ ነበር ድርሳነ ዑራኤል በሰፊው ይናገራል እመቤታችንም የኢትዮጵያ ሰዎች ባሳዩአት ፍቅር ስትደሰት ጌታችን የዐሥራት ሀገር ትሁንሽ ብሎ ሀገሪቱን ለእመቤታችን የሰጣት በወቅቱ የነበሩት ኢትዮጵያውያን ባሳዩት ደግነትና ርኅራኄ ነው፡፡ደጉ አባት አብርሃም እንግዳ በመቀበሉና ደግ በመሆኑ ሥላሴ ከቤቱ እንደ ገቡለት ሎጥም እንግዳ በመቀበል መላእክት ወደ ቤቱ ገብተው ሰዶምና ገሞራ ሲጠፉ ከጥፋት እንደታደጉት ጌታችን አባቶቻችን ባደረጉት ደግነት ኢትዮጵያ በእመቤታችን ምልጃ ሊጠብቃት ስለፈለገ የዐሥራት ሀገር አድርጎ ሰጣት ምን ጊዜም ሊምረው የወደደውን ሰው የእመቤታችን ፍቅር ያሳድርበታልና እመቤታችን እንድንወድ አድርጎ በአማላጅነቷ እንድንጠበቅ ፈቀደልን ጌታችን ወደ ግብፅና ወደ ኢትዮጵያ የተሰደደበት ምክንያት ለፍቅሩ ይሳሱለት ለነበሩት ኢትዮጵያና ግብፅ በፍቅር ለመገለጽ ሲሆን በተጨማሪም ገዳማተ ግብፅንና ገዳማተ ኢትዮጵያንም ለመባረክ ጭምር ነው፡፡በግብፅና በኢትዮጵያ ያሉ ታላላቅ ገዳማት የተባረኩት በስደቱ ወራት ነውና፡፡
ኪዳነ መልከ ጼዴቅን ለመፈጸም ነው፤መልከ ጼዴቅ ከዘመዶቹ ተለይቶ በምናኔ ሲኖር በሚያቀርበው መሥዋዕት በሚጸልየው ጸሎት በሥጋ ዘመዶቹ የሆኑትንና የማይዘመዱትን እንዲምርለት እግዚአብሔርን ይለምነው ነበር እንዲህ እያለ አቤቱ ለዲያብሎስ ከመገዛት ለአንተ ወደ መገዛት መልሰኸኛልና ከሀገሬም አውጥተህ አንተን ወደማመልክበት ቦታ አምጥተኸኛልና በደሌንም ይቅር ብለህልኛልና አመሰግንሃለሁ ነገር ግን እኔን ይቅር እንዳልከኝ ዘመዶቼንም ማርልኝ፡፡እግዚአብሔርም ልመናውን ተቀብሎ እንዲህ ሲል ድምፁን አሰምቶታል ልጄን ወደ ግብፅ በጠራሁት ጊዜ ዘመዶችህን እምርልሃለሁ ብሎ ቃለ ኪዳን ገብቶለት ነበር ዘመኑ ሲደርስ የተናገረውን የማያስቀር እግዚአብሔር የገባለትን ቃለ ኪዳን ለመፈጸም ወደግብፅ ተሰደደለት (ተረፈ ቄርሎስ ፳፭፥፩—፱) ኖኅ ከጥፋት ውኃ በኋላ መልአከ እግዚአብሔርን ከመካከላቸው እንደ ዳኛ አስቀምጦ ለሦስቱ ልጆቹ ለሴም ለካም ለያፌት ይህን ዓለም ቀኝ ቀኙን ለሴም መሀሉን ለያፌት ግራ ግራውን ለካም አውርሷቸዋል መልከ ጼዴቅ ትውልዱ ከካም ወገን ስለሆነ ምንም ዘመዶቼን ማርልኝ ብሎ የጸለየ ለሁሉም ዘመዶቹ ቢሆንም የአባቱ ወገኖች የካም ዘሮች ናቸውና ጌታ ወገኖቹን ሊምርለት ቃል ኪዳኑን ሊፈጽምለት ወደግብፅ ተሰዷል
.አጋንንትን ከግብፅና ከሰው ልቡና አስወጥቶ ለመስደድ ነው
ጌታ ገና ከመወለዱ በፊት ለልደቱ ሃያ አራት ቀን ሲቀረው መካነ ልደቱ ቤተ ልሔምን በመላእክት አስጠብቋት ነበር፡፡በዚህ ጊዜም አጋንንት በመላእክት ረቂቅ ጦር እየተወጉ ኢየሩሳሌምን ለቀው ሲወጡ የተሰደዱት ወደ ግብፅ ነበር አጋንንት በውስጣቸው አድርው ይመለኩባቸው የነበሩ ጣዖታትም ተሰባብረው ጠፍተዋል ይህንንም ጌታ ወደ ግብፅ በተሰደደ ጊዜ ራሳቸው አጋንንት በኢየሩሳሌም ማደሪያ እንዳሳጣኸን በዚህም ልታሳድደን መጣህን ብለው እንደ መሰከሩ በነገረ ማርያም ተጽፏል ጌታ ወደግብፅ የተሰደደበት ሦስተኛው ምክንያት እነዚህ አጋንንት ማደሪያ ካደረጓቸው የሰው ልቡናናና ከጣዖቱ አስወጥቶ በመስደድ አጋንንትን ለማሳደድ ነው፡፡ ይህንም ቴዎዶጦስ የተባለው ሊቅ ጌታ ተሰደደ ሲባል ብትሰማ ፍጡር ነው ብለህ አትጠራጠር ፈርቶ ሸሸም አትበል የጌታ መሰደድ ዲያብሎስን ከሰው ልቡና አስወጥቶ ለማሳደድ እንደሆነ እመን እንጅ ብሎ የተሰደደ ዲያብሎስን ለማሳደድ መሆኑን ገልጧል (ተረፈ ቄር፲፥፭)ይህ ሊቅ ጌታ የተሰደደው ዲያብሎስን ለማሳደድ ብቻ ሳይሆን ሰው መሆኑን ለሚጠራጠሩ፣ምትሐት ነው ለሚሉትም በትክክል ሰው መሆኑን ለማስረዳት እንደ ተሰደደ በዚሁ ምዕራፍና ቁጥር ይገልጻል ሰው ባይሆን ኑሮ አይሰደድም ነበር ፡፡
.አዳም ከዚህ ዓለም አፍአ በምትሆን ከገነት ተሰዶ ነበርና ለመካስ
ጌታችን በዕለተ ልደቱ የበለስ ቅጠል የለበሰ አህዮችና ላሞች እስኪያሟሙቁት ድረስ የተበረደ አዳም ከገነት ሲወጣ የበለስ ቅጠል ስለለበሰ ከልብሰ ብርሃን በመገፈፉ ስለተበረደ አዳም የተቀበለውን መከራ ተቀብሎ ለመካስ ነው፡፡ገና በሁለት ዓመቱ ከኢየሩሳሌም ወደግብፅ የተሰደደውም ከዚያው ሁኖ መዳን ተስኖት ሳይሆን አዳም ዕፀ በለስን በልቶ ከገነት እንደ ተሰደደ እሱም ከኢየሩሳሌም ወደ ምድረ ግብፅ ተሰዶ አዳም የተቀበለውን መከራ ተቀብሎ ለመካስ ነው፡፡አዳም ከገነት ወደ ማያውቀው ወደዚህ ዓለም ሲሰደድ ብዙ ፍዳና መከራ አግኝቶታል ፡ከአንዱ ቦታ ወደ አንዱ ቦታ በሚያደርገው እንቅስቃሴ እሾሁ ሲወጋው እንቅፋቱ ሲመታው ይህ ሁሉ የደረሰበት ከፈጣሪዉ ትእዛዝ በመውጣቱ መሆኑን ሲያስብ ዕንባው ከዓይኑ ያለማቋረጥ እንደምንጭ ውኃ ይፈስ ነበር፡፡
በገነት ሳለ የሚበላውና የሚጠጣው ከሰውነቱ ጋር ተዋሕዶ ይቀር ነበር እንጅ ወደ ኀሠርነት ስለማይለወጥ በልቶ ጠጥቶ መጨነቅ ሆድ ቁርጠት በልቶ መታመም በቁንጣን መሰቃየት አልነበረበትም ከገነት ከወጣ በኋላ ግን ይህ ሁሉ መከራ በርሱ ላይ መጥቶበታል ይህን ሁሉ መከራ ስለተቀበለ አዳም ወደዚህ ዓለም ሲሰደድ የተቀበለውን መከራ ተቀብሎ ሊክሰው ስለወደደ ወደ ግብፅ ተሰደደለት እንደተበረደ ተበረደለት በዕፀ በለስ ምክንያት ከገነት እንደወጣ በዕፅ ተሰቅሎ ያጣው ክብሩንና የክብር ቦታውን ገነትን መለሰለት
፭ ለሰማዕታት ስደትን ለመባረክ ፤ሰማዕትነት እሳትና ስለት ብቻ አይደለም ሀገርን ጥሎ መሰደድም ሰማዕትነት ነው፡፡ በመሆኑም ለሰማዕታት ስደትን ለመባረክ የማትችሉት መከራ ቢመጣባችሁ ተሰደዱ ለማለት ወደ ግብፅ ተሰደደ ስደት ከሰማዕትነት ገብቶ የተቆጠረበት ምክንያት መከራው በሰይፍ ተቆርጦ በስለት ተቀልቶ ከመሞት በላይ ስለሆነ ነው፡፡ከመከራ ሁሉ ከባዱ መከራም ደም ሳይፈስ በየጊዜው የሚፈጸመው የሰማዕትነት ተጋድሎ ነው በሰይፍ ተቀልቶ እሳት ውስጥ ገብቶ መሞት ቀላል ነው ባይባልም አስፈሪ ቢሆንም በስደት ልዩ ልዩ መከራ ከመቀበልና በየጊዜው ከመፈተን ግን የተሻለ ነው ሰይፍ የሚያስፈራው ለተወሰነ ደቂቃ ነው ስደት ግን በየጊዜው ከሰይፍ በላይ በሚያም መከራ መቆረጥና መሰቃየት ነው እመቤታችን በስደቷ ጊዜ ልጇ እንዳይሞትባት ከሰው ለመሰወር በበረሃው ስትሔድ ግሩማን አራዊት ያስደነግጧት ነበር ሰው ወዳለበት መንደር ስትሔድ ሰዎች ይጣሏታል፡፡
በዚያ ላይ ደግሞ ቀን ሐሩረ ፀሐዩ ሌሊት ቁረ ሌሊቱ እየተፈራረቀባት እሾሁ እየወጋት እንቅፋቱ እየመታት መውጫና መግቢያው በማይታወቅ በረሓ ውስጥ ገብቶ መሰቃየቱ የመንገዱ መጥፋት በዚያ አሰልችና አድካሚ ጉዞ ውስጥ የልጇ በውኃ ጥም መቃጠልና ማልቀስ ለእመቤታችን ሌላው ሰማዕትነት ነበር ይህን ሁሉ መከራ መቀበሏ ግን ሰማዕታትን በስደትና በልዩ ልዩ መከራ ሲሰቃዩ መከራውን እንዲችሉ ያደርጋቸዋል፡፡ለምን ይህ ሁሉ መከራ አገኘን ብሎ ተስፋ እንዳይቆርጡ ተስፋ ይሆናቸዋል ስለዚህ ለምን ይህ ሁሉ መከራ ደረሰብን ብለው ተስፋ እንዳይቆርጡ እመቤታችን ከተወደደ ልጇ ጋር ስደትን ባርካ ሰጠቻቸው እሷን መሠረት አብነት በማድረግም ብዙ ቅዱሳን ለሃይማኖታቸው ለቤተ ክርስቲያናቸው በስደትና በስለት መከራ ተቀበሉ ዋሻ ለዋሻ በረሓ ለበረሓ ተንከራተቱ ግን ተስፋ አልቆረጡም እመቤታችን መጽናኛ ሁናቸዋለችና ስለዚህ እመቤታችን በስለት ከሚፈጸመው መከራ ውጭ ያልተቀበለችው መከራ ስለሌለ እሞሙ ለሰማዕት የሰማዕታት እናታቸው እየተባለች ትመሰገናለች(ቅዳሴ ማርያም)
የቅዱሳንን ገድልና መከራ የሚናገረው ስንክሳር የቤተ ክርስቲያናችን መጽሐፍም ስደት እሳትና ስለት ብቻ አለመሆኑን እየተሰደዱ እየታሠሩ እየተገረፉ መከራ የሚቀበሉትን ቅዱሳን ሰማዕት ዘእንበለ ደም እያለ ይጠራቸዋል ሰማዕት ዘእንበለ ደም ማለትም ደማቸው ሳይፈስ ሰማዕትነትን የተቀበሉ ማለት ነው፡፡የእነዚህ ሰማዕታት ሰማዕትነት አንድ ጊዜ በማይገድል በየጊዜው በሚደርስ መከራ መሰቃየት ነውና፡፡
        በስደቷ ጊዜ ያገኛት መከራ
እመቤታችን ከተወደደ ልጇ ጋር በተሰደደችበት ጊዜ ልዩ ልዩ መከራ አግኝቷታል፡፡መከራውም ለእመቤታችን ኀዘን ጭንቅ ቢሆንም ለእኛ ግን ደስታና ድኅነት ነበር ምክንያቱም ከእመቤታችን በኋላ የነበሩ አባቶቻችንና የነርእሱ ልጆች የሆንነው እኛ ዛሬ ላይ ስደቷን መከራዋን እያሰብን የቻልን ሰውነታችን በጾም እያደከምን ያልቻልን ማኅሌት እየቆምን ለርሷና ለልጇ የምስጋና እጅ መንሻ እያቀረብን በስደቷ ወራት የደረሰባትን መከራ እያዘከርን እንድታማልደን እንማጸንበታለን በረከትም እናገኝበታለን፡፡ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴ ማርያም ድርሰቱ ላይ “አዘክሪ ድንግል ንግደቶ ዘምስሌኪ እንዘ ትጐይዪ ምስሌሁ እሀገር ለሀገር በመዋዕለ ሄሮድስ ርጉም አዘክሪ ድንግል አንብዐ መሪረ ዘውኅዘ እምአዕይንትኪ ወወረደ ዲበ ገጸ ፍቁር ወልድኪ አዘክሪ ድንግል ረኀበ ወጽምዐ ምንዳቤ ወኀዘነ ወኵሎ ዐፀባ ዘበጽሐኪ ምስሌሁ፤ርጉም ሄሮድስ በነገሠበት ወራት ከአንቺ ጋር ከአንዱ ሀገር ወደ አንዱ ሀገር የተሰደደውን መሰደድ አሳስቢልን በአይኖችሽና በልጅሽ ፊት የወረደውን መሪር ዕንባ አሳስቢልን ረሀቡን ጥሙን ችግሩንና ኀዘኑን ያገኘሽንም ልዩ ልዩ መከራ አሳስቢልን (ቅዳሴ ማርያም)በማለት እመቤታችን ሔሮድስ በነገሠበት ወራት ከአንዱ ሀገር ወደሌላው ሀገር መሰደዷን፣ ከዓይኗ የፈሰሰውንና በልጇ ፊት የወረደውን ዕንባ አማላጅ አድርጋ እንድታሳስብልን ይናገራል ይህንም ቃል ቅዳሴ ማርያም በተቀደሰበት ቀን ቤተ ክርስቲያናችን ሁልጊዜ ካህናቱ ሥጋውን ደሙን አቀብለው ከተመለሱ በኋላ ትጸልየዋለች እኛን ኀጥአንንም ታማልድበታለች፡፡
እመቤታችን በተሰደደችበት ወራት ካጋጠማት ጭንቅ ጭንቅ መከራ ሁሉ የሚበልጠው በልጇ ላይ የሚመጣው መከራ ነበር ምክንያቱም ሀገር ጥላ የተሰደደችው ተወዳጁን ልጇን ከሞት ለማዳን ነውና፡፡ሄሮድስ አራት ወታደሮችን ከነሠራዊታቸው በሽልማት ሸልሞ እመቤታችን ከነልጇ ይዘው ከመጡ የበለጠ ሹመትና ሽልማት እንደሚጠብቃቸው አብስሮ ልኳቸው ነበር፡፡
የዮሴፍ ልጅ ዮሳ ይህንን ምስጢር ለአባቱ ለዮሴፍና ለእመቤታችን እንዲሁም ለሰሎሜ ለመንገር ከነበረው ኃይል ላይ የአንበሳ ኃይል ተጨምሮለት በፍጥነት ሲጓዝ እያለ የመልካም ነገር ጠላት የሆነው ሰይጣን መንገድ ላይ ጠብቆ ወዴት እንደሚሔድ ጠየቀው ዮሳም በየዋህነት የሚሮጥበትን ጉዳይ ሳይደብቅ ዘርዝሮ ነገረው ሰይጣንም የሄሮድስ ሠራዊት ቀድመው መሔዳቸውን በሔዱበት ፍጥነት ካገኟቸው እንደሚገድሏቸው ዮሳም በከንቱ እንዳይደክም ያዘነ በሚመስል ድምፅ እንዲመለስ ነገረው ዮሳ ግን ሐሳቡን ሳይቀበል ከሞቱም እቀብራቸዋለሁ በሕይወት ካሉም የሆነውንና የታሰበውን ነግሬ እንዲሸሹ አደርጋለሁ ብሎ መገስገስ ጀመረ ኃይል ከእግዚአብሔር ተጨምሮለታልና፡፡
ዮሳ እየሮጠ ሲሔድ መንገድ ላይ አገኛቸውና ገና ከመድረሱ እመቤታችን ያስደነገጠ ሕሊናዋን የረበሸ ምርር ብላም እንድታለቅስ የሚያደርግ አሰቃቂ ዜናን ነገራት እመቤታችንም የዮሳን ቃል ሰምታ ከአንዱ ሀገር ወደ ሌላኛው ሀገር የተሰደድኩት ከሞት ላላድንህ ነውን? ልጄ አንተን ሲገሉህ ከማይ እኔ አስቀድሜ ልሙት በማለት ስታለቅስ ሕፃኑ ኢየሱስ ክርስቶስ በእጁ ዕንባዎቿን በማበስ እንደማይሞት ከነገራት በኋላ ፊቱን ወደ ዮሳ መልሶ ዮሳ ዕሡይ ምጽአትከ (አመጣጥህ ዋጋ የሚያሰጥ መልካም) ነበር ነገር ግን እናቴን አስደንግጠሃታልና በዕለተ ምጽአት አስነሥቼ ዋጋህን እስከሰጥህ ድረስ ይህችን ደንጋይ ተተንተርሰህ ዕረፍ ብሎት ዐርፋል፡፡
እንግዲህ እመቤታችን በስደቷ ወራት ውኃ በመጠማት በመራብ እሾሁ እየወጋት እንቅፋቱ እየመታት ቀን የበረሓው ሐሩር እያቃጠላት ሌሊት ደግሞ ብርዱ እያሳቃያት ትጓዝ ስለነበር ያገኛትን መከራ በቃላት ገልጾ መጨረስ አይቻልም በተለይ ሰው ስታይ ልጇን የሚገድሉባት ስለሚመስላት በጣም ትጨነቅም ታለቅስም ነበር፡፡
አባ ሕርያቆስም በስደትሽ ወራት ያገኘሽን ልዩ ልዩ መከራ ከልጅሽ ዘንድ አሳስቢልን ያለው ያገኛትን መከራ አስባ እኛንም ከአስፈሪ ፈተና እንድታወጣን ነው አባቶችም እመቤታችን መከራዋን እያነሡ ካለቀሱና ከለመኗት ፈጥና እንደምትሰማ በሕይወታቸው ካገኙት ተሞክሮ ተነሥተው ይናገራሉ፡፡ስለዚህ እኛም በወርኀ ጽጌ ስደቷን ስናስብ የራሳችንንም የሀገራችንንም ችግር አብረን ልናስብ ይገባል፡፡በተለይ በሀገር የሚመጣ ችግር ለሁላችንም የሚተርፍ ስለሆነ እመቤታችን የዐሥራት ሀገሯን በአማላጅነቷ እንድትጠብቃት ሁላችንም የቻልነውን ያህል በወርኀ ጽጌ ተግተን ልንጸልይ ማኅሌት ልንቆም በጸሎት ልንበረታ ይገባል አምላካችን እግዚአብሔር የሀገራችን ጥፋት አያሳየን አሜን፡፡
ምንጭ፤ሐመር መጽሔት ፳፮ኛዓመት ቊ ፮ ጥቅምት ፳፻፲ወ፩ ዓ.ም

ኢየሱስ ስዱድ ተስፋሆሙ ለስዱዳን፤ ስደተኛው ኢየሱስ የስደተኞች  ተስፋቸው ነህ (ሰቆቃወ ድንግል)

                                                            በመጋቤ ሐዲስ በርሄ ተስፋ መስቀል

መጽሐፍም ታሪክም እንደሚነግረን በዓለም ብዙ ዓይነት ስደት አለ። ሁሉም ስደቶች ግን የአዳምንና የሔዋንን ስደት ተከትለው የመጡ ናቸው። ቀደምት ወላጆቻችን ሕገ እግዚአብሔርን ባፈረሱ ጊዜ ከገነት ተሰደው ምድረ ፋይድ ወርደዋል (ዘፍ. ፫፥፩፥፲፩)፡፡ ከዚህ በኋላ ከቦታ ወደ ቦታ መሰደድና መንከራተት የሰው ልጅ ዕጣ ፈንታ ሆኗል። በዘመነ ብሉይ የነበሩት ስደተኞችና በምርኮ የተያዙ ሁሉ ስደታቸውን በሚጠት የሚፈፅም፣ ኀዘናቸውን በደስታ የሚለውጥ አንድ መሢሕ እንደሚመጣ በተስፋ ይጠባበቁ  ነበር (መዝ. ፹፬፥፬፣ ሰቆቃወ ኤርምያስ. ፭፥፳፩)፡፡

ሊቁ አባ ሕርያቆስ “አንቲ ውእቱ ተስፋሁ ለአዳም አመ ይሰደድ እምገነት፤ አዳም አባታችን ከገነት በተሰደደ ጊዜ ተስፋው አንቺ  ነሽ” በማለት መናገሩ የአዳምና የሔዋን ሚጠት ማለት ወደ ቀደመው ክብር – ወደ ገነት መመለስ ድንግል ማርያም በወለደችው በክርስቶስ እንደሚሆንና ድንግል  ማርያምም ምክንያተ ድኅነት መሆኗን ለመግለጥ ነው።

በዘመነ ሐዲስም ቢሆን ጽድቅን ፍለጋ የሚሰደዱ እንዳሉ ሁሉ እንጀራን ፍለጋ ሀገር ጥለው ከወገን ርቀው የሚሰደዱ መከራና ግፍ የሚደርስባቸው ክርስቲያኖች አሉ። የእነዚህም ተስፋቸው  ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ለዚህም ነው ስድተኞቹ በየሔዱበት ዓለም እየተሰባሰቡ የአምልኮ ሥርዓታቸውን የሚያካሔዱት። ይህን በመንፈስ ቅዱስ ምሪት የተገነዘቡት አባ ጽጌ ድንግል “ኢየሱስ ስዱድ ተስፋሆሙ ለስዱዳን ፥ ኢየሱስ  ግፉእ ተስፋሆሙ ለግፉአን”  በማለት  የተናገሩት።

ወደ ዋናው አሳባችን እንመለስና የባሕርይ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ከድንግል ማርያም በቤተ ልሔም በተወለደ ጊዜ ሰብአ ሰገል ኮከብ እየመራቸው ­“የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው” እያሉ ወደ ኢየሩሳሌም መጡ (ማቴ. ፪፥፪)፡፡ ሰብአ ሰገል /የጥበብ ሰዎች ለምን ክርስቶስን የአይሁድ ንጉሥ ብለው ጠሩት? የሚል ይኖራል፦ ስም ላዕላዊ፣ ስም ማዕከላዊ፣ ስም ታሕታዊ የሚባል አለ። ስለዚህ

  • በስም ላዕላዊ – “አይቴ ሃሎ አምላክ /ፈጣሪ ዘተወልደ” ቢሏቸው ምን ሞኞች ናቸው ሰማይና ምድር የማይችሉትን እንዴት ተወለደ ይላሉ ባሏቸው ነበር።
  • በስም ታህታዊ – “አይቴ ሃሎ ሕፃን ዘተወልደ” ቢሏቸው ምን ሞኞች ናቸው በእስራኤል የተወለደው ስንት ሕፃን አለ ስንቱን እናውቃለን? ባሏቸው ነበርና፣
  • ስም ማእከላዊን ወስደው – “አይቴ ሃሎ ንጉሠ እስራኤል ዘተወልደ፤ የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው?” – ቢሏቸው ሄሮድስ ምድራዊ ንጉሥ መስሎት ንጉሥማ ንጉሥን ሳይሽር ይነግሣልን ብሎ ደንግጧል (ማቴ. ፪፥፫)፡፡

ወንጌላዊው ማቴዎስ እንደ ጻፈልን ሰብአ ሰገል ጌታን ከእናቱ ከድንግል ማርያም ጋር ባገኙት ጊዜ ወድቀው ሰገዱለት ፥ እጅ መንሻውንም አቀረቡለት (ማቴ. ፪፥፪-፲፩) ዓይነቱም ወርቅ ፥ ዕጣን፣ ከርቤ  ነው። የቀረበው እጅ መንሻ እንዲህ መሆኑም ያጋጣሚ ጉዳይ ሳይሆን ምሥጢር አለው።

  • ወርቅ አመጡለት፦ ወርቅ ስንገብርላቸው የነበሩ ነገሥታት ቀድሞም ፍጡራን ኋላም ኃላፍያን ናቸው ፥ አንተ ግን ቀድሞም ያልተፈጠርክ ፥ በኋላም የማታልፍ ዘለዓለማዊ አምላክ ነህ ሲሉ ወርቅ አመጡለት። በተጨማሪም ወርቅ ጽሩይ እንደሆነ አንተም ጽሩየ ባሕርይ ነህ ለማለት ወርቅ አመጡለት።
  • ዕጣን አመጡለት ይህን ስናጥናቸው የነበሩት ጣዖታት ጥንቱም ፍጡራን ፥ ኋላም ኃላፍያን ናቸው ፥ አንተ ግን ቀድሞም ያልተፈጠርክ ኋላም የማታልፍ ነህ ሲሉ ዕጣን አመጡለት። በሌላ አገላለጽ ዕጣን ምዑዝ ነው አንተም ምዑዘ ባሕርይ ነህ ሲሉ ነው።
  • ከርቤ አመጡለት፦ ምንም ቀድሞ ያልተፈጠርክ በኋላም የማታልፍ ብትሆን ለሰው ስትል ፈቅደህ በተዋሐድከው ሥጋ የፈቃድ ሞትን መቀበል አለብህ ሲሉ ከርቤ አመጡለት።

በተጨማሪም ከርቤ የተሰበረውን እንዲጠግን ፥ የተለያየውን አንድ እንዲያደርግ አንተም ከማኅበረ መላእክት የተለየውን አዳምን ጽንዐ ነፍስን ሰጥተህ ወደ ቀደመ ቦታው ትመልሰዋለህ ሲሉ ከርቤ አመጡለት –  በማለት  ሊቃውንት ተርጉመዋል (ትርጓሜ ወንጌለ ማቴዎስ. ፪፥፲፩)፡፡ አዳምን ወደ ቦታው ለመመለስ ከተደረጉ የማዳን ሥራዎች መካከል የጌታ ስደት አንዱ ነው።

ኢትዮጵያዊው ሊቅ አባ ጊዮርጊስ መጽሐፈ ምሥጢር በተባለው ድርሰታቸው፦ “በዚያ በጽርሐ አርያም የሚደነቅ ከማይታይ አብ የመወለድ ምስጋና አለው ፥ በዚህም በቤተ ልሔም ከድንግል መወለድ ምስጋና አለው። በዚያ ከሰማያውያን ካህናት በወርቅ ማዕጠንት የዕጣኑን መዐዛ ይቀበላል ፥ በዚህም ወርቅንና ከርቤን ዕጣንንም ከሰብአ ሰገል ተቀበለ” በማለት ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል (ሉቃ. ፪÷፩-፲፯፣ ራእይ. ፰÷፰-፬፣ ማቴ. ፪÷፲፩፣ መጽሐፈ ምሥጢር ገጽ. ፷፰-፸)፡፡

የጥበብ ሰዎች የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው? ባሉት ጊዜ ሄሮድስ በጉዳዩ ሰግቶ ሰብአ ሰገልን “ሒዱ ፥ ስለ ሕፃኑ በጥንቃቄ መርምሩ፤ ባገኛችሁትም ጊዜ እኔ ደግሞ መጥቼ  እንድሰግድለት ንገሩኝ” ብሏቸው እንደ ነበር እናስታውሳለን (ማቴ. ፪፥፰)፡፡ ምንም እንኳ ኢየሱስ  ክርስቶስ ነገሥታት የሚሰግዱለት የባሕርይ ንጉሥ መሆኑ እውነት ቢሆንም ነገር ግን ሄሮድስ  መጥቼ እንድሰግድለት ማለቱ በተንኮል ነበር። ስለዚህም የጥበብ ሰዎች ወደ ሄሮድስ እንዳይመለሱ  በሕልም ተረድተው በሌላ መንገድ ወደ ሀገራቸው ሔዱ (ማቴ. ፪፥፲፪)፡፡

ከዚያ በኋላ ነው መልአኩ ለዮሴፍ በሕልም ተገልጾ – “ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ተነሣ ሕፃኑንና እናቱንም ይዘህ ወደ ግብፅ ሸሽ ፥ እስክነግርህም ድረስ በዚያ ተቀመጥ” በማለት የተናገረውና ጻድቁ ዮሴፍ ሕፃኑንና እናቱን ድንግል ማርያምን ይዞ በሌሊት ወደ ግብፅ የተሰደደው (ማቴ. ፪፥፲፫) ሄሮድስም ሰብአ ሰገል እንደ ተሳለቁበት ባወቀ ጊዜ የአይሁድ ንጉሥ ኢየሱስ ክርስቶስን ያገኘ መስሎት እጅግ ብዙ ሕፃናትን ፈጅቷል (ማቴ. ፪፥፲፮)፡፡ ጌታችን ግን ጊዜው ሳይደርስ ደሙን ሊያፈስ ፥ ሊሞትም አይገባምና ከሄሮድስ ፊት ያመልጥ ዘንድ ከእናቱ ጋር ተሰዷል።

ኢየሱስ ክርስቶስ ለምን ተሰደደ፤ ለምንስ ስደቱን ወደ ግብፅ አደረገው?

ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደበት ምክንያት እንዳለው ሁሉ የተሰደደበት እና ስደቱን ወደ ምድረ ግብፅ ያደረገበት ምክንያትም አለው። ይኸውም፡-

  • ትንቢተ ነቢያትን ለመፈጸም ነው፣

የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ በዘመነ ሥጋዌው ያደረጋቸው ነገሮች በሙሉ አስቀድሞ በልብ የመከረውን ፥ ኋላም በነቢያት ያናገረውን ለመፈፀም እንጂ በአጋጣሚ የተከናወኑ አይደሉም። ወደ ግብፅ እንደሚሰደድም ትንቢት ተነግሮለት ነበር። “ከጌታ ዘንድ በነቢይ፦ ልጄን ከግብፅ ጠራሁት የተባለው እንዲፈጸም ወደ ግብፅ ሔደ ፥ ሄሮድስም እስኪሞት ድረስ በዚያ ኖረ” (ማቴ. ፪፥፲፬-፲፭) እንዲል፡፡ ነቢያት ትንቢታቸውን ሲናገሩ የጌታችንን መሰደድ ብቻ ሳይሆን ከማን ጋር ፥ ወዴት እንደሚሰደድ፣ በስደቱ ጊዜ ምን ምን እንደሚሠራ በግልፅ አስቀምጠውታል። የክርስትናን  አስተምህሮ እርግጠኛ የሚያደርገውም ይህ ነው።

ከነቢያቱ መካከል ነቢዩ ኢሳይያስ መንፈሰ እግዚአብሔር መርቶት ቅድስት ድንግል ማርያም የባሕርይ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስን ይዛ ወደ ምድረ ግብፅ እንደምትሰደድ “እነሆ እግዚአብሔር በፈጣን ደመና እየበረረ ወደ ግብፅ ይመጣል” (ኢሳ. ፲፱፥፩) በማለት ተናግሯል። ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ድንግል ማርያምን “አፍጣኒተ ረድኤት ማርያም በጊዜ ምንዳቤ ወአጸባ ለዓይን እምቀራንባ፤ በኀዘንና በችግር ጊዜ ሰውን ለመርዳት ከዓይን ጥቅሻ ይልቅ ድንግል ማርያም ፈጣን ናት” እያለች የምታመሰግነው ለዚህ ነው። ይህን የኢሳይያስን ትንቢት ሁለት ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት እንደሚከተለው አመስጥረው ተርጉመውታል፡፡

  • ቅዱስ ያሬድ

መዓዛ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ያሬድ “… ኢሳይያስ ነቢይ ፥ ልዑለ ቃል እም ነቢያት ከልሐ ወይቤ እግዚአብሔር ጸባኦት ይወርድ ብሔረ ግብፅ፤ ከነቢያት ይልቅ ድምፁ ከፍ ያለው ነቢዩ ኢሳይያስ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ወደ ግብፅ ምድር ይወርዳል ብሎ አሰምቶ ተናገረ። – ደመና ቀሊል ዘይቤ ኢሳይያስ ይእቲኬ ማርያም ድንግል እንተ ጾረቶ በከርሣ ለወልደ እግዚአብሔር፤ ኢሳይያስ ፈጣን ደመና ብሎ የተናገረላትም የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጁን በማሕፀኗ የተሸከመችው ድንግል ማርያም ናት” (መዋሥዕት) በማለት አብራርቶታል፡፡

  • አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ

ዐምደ ሃይማኖት የተሰኘው ቅዱስ አባ ጊዮርጊስም “ሄሮድስ ኃሠሠ ዘኢይትረክብ ወእግዚእ ተግሕሠ ውስተ ምድረ ግብፅ ፥ ተጽዒኖ ዲበ ደመና ቀሊል ፥ በከመ ይቤ ኢሳይያስ – ናሁ እግዚአብሔር ይወርድ ውስተ ምድረ ግብፅ ተጽዒኖ ዲበ ደመና ቀሊል ፥ ደመናሰ ቀሊል አንቲ ክመ ኦ ቅድስት ድንግል፤ ሄሮድስ የማያገኘውን ፈለገ ጌታም በፈጣን ደመና ተጭኖ ወደ ግብፅ ምድር ሔደ ፥ ነቢዩ ኢሳይያስ እነሆ እግዚአብሔር በፈጣን ደመና ተጭኖ ወደ ግብፅ ምድር ይወርዳል ብሎ እንደ ተናገረ፥ ቅድስት ድንግል ሆይ ፈጣን ደመና መቼም መች ቢሆን አንቺ ነሸ። … እግዚአብሔር ተአንገደ ውስተ ምድረ ግብፅ ተሐዚሎ በዘባን፤ … እግዚአብሔር በጀርባሽ ታዝሎ በግብፅ ምድር እንግዳ ሆነ” (አርጋኖን ዘሰኑይ) እንዲል፡፡

የተከበራችሁ አንባብያን ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን እግዚአብሔርን የምታገለግልባቸው፥ ምእመናንን የምታስተምርባቸው ድርሳናት እንዳሏት እሙን ነው። እነዚህ ሁሉ መሠረታቸው መጽሐፍ ቅዱስ መሆኑንም ከሁለቱም ሊቃውንት ልናስተውል ይገባል። ከዚህ የተነሣ የማኅሌቱ፣ የቅዳሴውና የሰዓታቱ መሠረት መጽሐፍ ቅዱስ ነው ብለን መናገር እንችላለን። በሌላ አገላለጽ ድርሳናት ገድላት መደበኛ ሥራቸው ረቂቅ ምሥጢር የሆነውን መጽሐፍ ቅዱስ ማመሥጠር፥ ማብራራት ፥ መተርጎም መሆኑን ከሊቃውንቱ ድርሰት ተምረናል። ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን  ትምህርቷ ምሉእ ፥ እምነቷ ርቱዕ የሆነውም በዚህ ምክንያት ነው።

አምልኮ ጣዖትን ለማጥፋት ነው

ጌታችን ወደ ግብፅ የተሰደደበት ምክንያት አለው ያልነው እዚህ ላይ ይገለጻል። ይኸውም በዚያ ጊዜ ግብፃውያን ክሕደት ወይም አምልኮ ጣዖት ጸንቶባቸው ነበርና ይህን ክፉ አምልኮ ጣዖት ለማጥፋት፣ ለመደምሰስ ክርስቶስ ስደቱን ወደ ግብፅ አድርጎታል። ታላቁ ነቢይ ኢሳይያስ “እነሆ እግዚአብሔር በፈጣን ደመና እየበረረ ወደ ግብፅ ይመጣል።” ካለ በኋላ ዓላማውን ሲገልጽ  “የግብፅም ጣዖታት በፊቱ ይርዳሉ” ብሏል (ኢሳ. ፲፱÷፩)፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድም ጌታችን ወደ ግብፅ የተሰደደበትን ምክንያት ሲያስረዳ እንዲህ ብሏል፡- ይፈጽም ትንቢተ የሐድስ ብሊተ፤ ይክሥት  መንክራተ ፥ ዘሀሎ መልዕልተ፤ ለቢሶ ስብሐተ ፥ ብሔረ ግብጽ ቦአ ይሥዐር ጣዖተ፤ ወይንሥት ኵሎ ግልፍዋተ፤ ትንቢትን ይፈጽም ዘንድ፣ አሮጌውንም ያድስ ዘንድ፣ በላይ ያለውን ድንቅ ነገር  ይገልጥ ዘንድ፣ ምስጋናን ተጎናጽፎ ጣኦታትን ሊሽር፣ ምስሎችንም ሁሉ ሊያፈርስ ወደ ግብፅ ምድር ገባ /ድጓ ዘበአተ ግብፅ/ ሌላው ኢትዮጵያዊው ሊቅም ሰቆቃወ ድንግል በተሰኘው ድርሳኑ ድንግል ማርያምን ከታቦተ ጽዮን ጋር በማነጻጸር እንዲህ  ብሏል፡-

ታቦተ አምላክ እስራኤል ጽዮን ዘነገደት ምድረ ኢሎፍሊ፤ ወቀጥቀጠቶ ለዳጎን ነፍሳተ ብዙኅን ማህጎሊ፤ አመ ነገደት ቍስቋመ በኅይለ ወልደ ከሃሊ፤ ወድቁ አማልክተ ግብጽ መናብተ ሰይጣን ሐባሊ፤ ወተኅፍሩ ኵሎሙ ዘቦሙ አስጋሊ። ወደ ኢሎፍሊ ምድር ተማርካ የሄደች የእስራኤል አምላክ የቃል ኪዳኑ ታቦት ታቦተ ጽዮን፥ የብዙዎችን  ነፍሳት ያጠፋ ዳጎንን  ሰባበረችው። ድንግል ማርያምም ሁሉን ማድረግ በሚችል  ልጇ   ግብፅ ወደሚባል ሀገር በሔደች ጊዜ የሐተሰኛ ሰይጣን ዙፋኖች የሆኑ የግብፅ ጣዖታት ፈረሱ ፥ ጠንቋይ  አስጠንቋይ ያላቸው ሁሉ  ዐፈሩ (ሰቆቃወ ድንግል)፡፡

ከዚህ የምንረዳው የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ስደት ተራ ስደት ሳይሆን ሰዎችን ከአምልኮ ጣዖት ወደ አምልኮቱ ማለትም ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር ለማምጣት የተደረገ  መሆኑን መረዳት ተገቢ ነው። ስለዚህ  ጌታ  በስደቱ  ሰዎችን ከክህደት አድኗል ማለት ነው።

  • ስደትን ለሰማዕታት – ለቅዱሳን ሁሉ ባርኮ ለመስጠት

መልካም እረኛ በበጎቹ ፊት ይሔዳል። “የራሱንም ሁሉ ካወጣቸው በኋላ በፊታቸው ይሔዳል ፥ በጎቹም ድምፁን ያውቃሉና ይከተሉታል፤” (ዮሐ. ፲፥፬) እንዲል፡፡ መልካሙ እረኛ ክርስቶስ ሲሆን በጎች የተባሉትም ደጋጎቹ ምእመናን ናቸው። በፊታቸው ይሔዳል ሲል፡- ኢየሱስ ክርስቶስ መምህር፥ መሪ እንደ መሆኑ መጠን ምእመናንን ይመራቸዋል እንጂ በኋላ ሆኖ አይነዳቸውም። ይህ ማለት እኛ ክርስቲያኖች ልናደርጋቸው የሚገቡ ነገሮችን በሙሉ እርሱ አስቀድሞ በተግባር ፈጽሞ አሳይቶናል። ስለዚህ የክርስቲያኖች ትክክለኛው አርአያ አብነት ክርስቶስ ነው። መጠመቁን አብነት አድርገን ተጠምቀናል (ማቴ. ፫፥፲፮-፲፯)፣ መጾሙን አብነት አድርገን እንጾማለን (ማቴ. ፬፥፩-፲)፣ የምንጸልየው መምህራችን ኢየሱስ ክርስቶስ  በጌቴሴማኒ ስለ ጸለየ ነው (ማቴ. ፳፮-፵፩)፣ ጠላታችንን ይቅር ማለት ያለብን ክርስቶስን አብነት አድርገን ነው። (ቆላ. ፫፥፲፫)፤በፊት መሔድ ማለት ለመልካም  ነገር  ሁሉ  አብነት  አርአያ መሆን  ማለት ነው።

እንደዚሁ ሁሉ በመሰደዱ ምክንያት ስለ ጽድቅ ብለው ለሚሰደዱ ቅዱሳን፣ መናንያን ባሕታውያን ሁሉ አብነት ሆኗል። ጥምቀታችንን፣ ጾም ጸሎታችንን እንደ ባረከ ሁሉ፥ ስደቱንም ባረኮ ጀምሮ ሰጥቶናል። ለዚህም ነው “ስለ ጽድቅ የሚሰደዱ ብፁዓን ናቸው ፥ መንግሥተ ሰማያት የእነርሱ ናትና።” (ማቴ. ፭፥፲) በማለት የተናገረው፡፡

ጻድቃን ፥ ሰማዕታት በአጠቃላይ ቅዱሳን ሁሉ ክርስቶስን ተስፋ አድርገው ሀብትን ንብረትን ትተው ፥ ዓለምን ንቀው ተሰደዋል። ክርስቶስ በስደቱ ጊዜ ብዙ መከራዎችን እንደ ተቀበለ ቅዱሳንም  በዓላውያን ነገሥታት፣ ክፋት በጸናባቸው ሰዎች እጅግ ብዙ መከራን ተቀብለው ተሰደዋል። በዚህም ዋጋቸውን አግኝተዋል። ስለዚህ እራሱ ባርኮ ባይሰጠን ኖሮ ስደትን ማንም አይችለውም ነበር።

ከዚህ ሁሉ መረዳት የሚቻለው ክርስቶስ አብነት ያልሆነበት የጽድቅ፣ የበረከት ሥራ እንደሌለ ነው። ይህ ማለት ኢየሱስ ክርስቶስ ክርስቲያኖች ሊያደርጓቸው የሚገቡ መልካም ነገሮችን ሁሉ አስቀድሞ አድርጓቸዋል። በመሆኑም ክርስቲያኖች ሁሉ እረኛችንን ክርስቶስን አውቀን፣ ድምፁንም ለይተን በመረዳት በመልካም ነገር ሁሉ እረኛችንን ክርስቶስን እንመስል ዘንድ ይገባናል ማለት ነው።

  • ወደ ቀደመው ርስታችን ሊመልሰን ተሰዷል

ከላይ እንደ ተገለጠው የመጀመሪያው ስደተኛ አዳም ነው። በመቀጠልም ልጆቹ ሁሉ ስደተኞች ሆነዋል። ስለዚህ ዳግማይ አዳም ክርስቶስ የተሰደደው አዳምንና ልጆቹን ፍለጋ ነው (ሉቃ. ፲፭፥፩-፱)፡፡ ከዚህ በመነሣት ነው ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ “…ዘሐሰሶ ለበግዕ ግዱፍ ወሶበ ረከቦ ፆሮ ዲበ መትከፍቱ፤ የጠፋው በግ አዳምን የፈለገው ፥ ባገኘውም ጊዜ በትክሻው የተሸከመው እውነተኛ እረኛ” /ሃይማኖተ አበው ዘዮሐንስ አፈወርቅ/ በማለት የተናገረው። ከዚህ አኳያ የቀዳሚት ሔዋን ስደትም በዳግማዊት ሔዋን ድንግል ማርያም ስደት ተክሷል፡፡

መልአከ እግዚአብሔር ዮሴፍ ድንግል ማርያምን ይዞ እንዲሰደድ እንደ ነገረው ሁሉ ሦስት ዓመት ከስድስት ወራት ከሆናቸው በኋላ መልአኩ እንደገና “የሕፃኑን ነፍስ የፈልጉት ሞተዋልና ተነሣ ፥ ሕፃኑን እናቱንም ይዘህ ወደ እስራኤል ሀገር ሒድ” (ማቴ. ፪፥፳) በማለት ነግሮታል፡፡ ልብ በሉ ገዳዩ ሞተ ፥ ሊገደል የታሰበው ሕያው ሆነ። ዮሴፍም ሕፃኑን ክርስቶስን ከእናቱ ከድንግል ማርያም ጋር እንደ ተሰደደ ይዟቸው ወደ እስራኤል ተመልሶ ገባ (ማቴ. ፪፥፳፩) መንግሥተ ሰማያት የሚገቡት እነማን ናቸው ቢሉ ጌታን ከእናቱ ጋር የያዙት ናቸው።

ማጠቃለያ

የጌታችን ስደት ጠላታችን ዲያብሎስ ከሰዎች ልብ ወጥቶ እንዲሰደድ ያደረገ በመሆኑ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሚገባ ታከብረዋለች፡፡ ለዚህም ነው ሊቃውንቱ “ጕየተ ሕፃን አጕየዮ ለዲያብሎስ፤ የሕፃኑ ስደት ዲያብሎስን እንዲሸሽ አድርጎታል” በማለት የሚገልጡት።የተከበራችሁ የልዑል እግዚአብሔር ወዳጆች! ድንግል ማርያም ልጇን ወዳጇን ኢየሱስ ክርስቶስን ይዛ፣ ዮሴፍንና ሰሎሜን አስከትላ ከእስራኤል እስከ ግብፅ፥ ከዚያም እስከ ኢትዮጵያ በመሰደድ ለሦስት  ዓመት ከስድስት ወር እጅግ ብዙ መከራን ተቀብላለች (ራእ. ፲፪፥፩-፮፤ ፲፬-፲፰)፡፡

 አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ “እወ አማን እምውሉደ ሰብእ አልቦ ፥ ምንዳቤ ወግፍእ ዘከማኪ በውስተ ዓለም ዘረከቦ፤ ድንግል ሆይ! አዎን በእውነት ከሰው ልጆች መካከል በዚህ ዓለም እንደ አንቺ ችግርና መከራ የደረሰበት የለም” በማለት እንደመሰከሩት መከራዋም ልዩና እጅግ ብዙ ነው። በዚህም ድንግል ማርያም በነገረ ድኅነት ውስጥ የማይተካ ሚና ያላት መሆኑን መረዳት ይገባል። በተጨማሪም እናቶች ለልጆቻቸው ምን ያህል መሥዋዕትነት መክፈል እንዳለባቸው ያስተማረች የሕይወት  መምህር መሆኗን መገንዘብ ብልህነት ነው። የጌታ ስደት ስደታችንን፣ ሚጠቱ ሚጠታችንን የሚያመለክት ነው። በሌላ አገላለጥ የድንግል ማርያም ስደት የሔዋንን ስደት፣ ሚጠቷም እናታችን ሔዋን በዳግማዊት ሔዋን በድንግል ማርያም መመለሷን ያሳያል። የዮሴፍና የሰሎሜ ስደት የደቂቀ  አዳም ሁሉ ስደትን የሚያሳይ ሲሆን ሚጠታቸውም የአዳም ዘር ሁሉ በክርስቶስ የማዳን ሥራ ወደ ቀደመው ክብራችን፣ ወደ ገነት መመለሳችንን ያመለክታል። እንዲህም ስለሆነ ግብፅ የሲኦል ምሳሌ ፥ ኢየሩሳሌምም የገነት ምሳሌ ናት፡፡ በዚህ መሠረት ኢየሱስ ክርስቶስ ከእስራኤል ወደ ግብፅ ተሰዶ እንደገና ወደ እስራኤል መመለሱ፥ ከገነት የተሰደደው አዳም በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስደትና አጠቃላይ የማዳን ሥራ ወደ ጥንተ ክብሩ መመለሱን የሚያጠይቅ ነው። እግዚአብሔር ከተሰደድንበት የጽድቅ ሥራ በንስሓ ይመልሰን፥ የድንግል እናቱን በረከትና ረድኤት ያድለን።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ፳፮ኛዓመት ቁ፪/ቅጽ ፳፮ ቁጥር ፫፻፺፭ ከጥቅምት፩-፲፭ ቀን፳፻፲ወ፩ ዓ.ም