ከሰላም የምታደርሰንን መንገድ እንያዝ

 

ብዙዎቻችን ስለ ሰላም እንናገራለን እንጂ ሰላም በውስጣችን አለመኖሩን የሚያሳዩ ተግባራትን ስንፈጽም እንታያለን፡፡ ሰላም የምንሻ ከሆነ ሰላማውያን ከመሆን በተጨማሪ ሌሎችም ሰላማውያን እንዲሆኑ የምንችለውን ሁሉ ማድረግ ይኖርብናል፡፡ ከጥፋት ልንድን ብቻ ሳይሆን ሌሎችን ከጥፋት ልንታደግ እንደሚገባ “ወንድሞቻችን ሆይ ከእናንተ ከጽድቅ የሳተ ቢኖር ከኃጢአቱ የመለሰውም ቢኖር ኃጢአተኛውን ከተሳሳተበት መንገድ የሚመልሰው ራሱን ከሞት እንዳዳነ ብዙ ኃጢአቱንም እንደአስተሰረየ ይወቅ” (ያዕ. ፭፥፲-፱፳) በማለት ቅዱስ ያዕቆብ አስተምሮናል፡፡

ሰላም በስምምነት፣ በአንድነት፣ በፍቅር የምንኖርበት የዕረፍት እና የተስፋ ስሜት የተሞላበት ሕይወት ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት ሰላምን እንከተላት ዘንድ የሚያሳስበንም ሰላም ጥቅም እንጂ ጉዳት የሌለባት በመሆኑ ነው፡፡ ሰላማዊ ሰው ማንም ያሳድደኛል ብሎ ሳይሰጋ ተረጋግቶ ይኖራልና፡፡ በእጁ ጥፋት በሕሊናው በደል ስለሌለበትም ደስተኛ ሆኖ ይኖራል፡፡ ክርስቲያኖች ሰላማዊ የሚሆኑትም የሰላምን ንጉሥ ኢየሱስ ክርስቶስን ስለሚከተሉ ነው፡፡ ክርስቲያኖች ብርሃናቸው በሰው ፊት የሚገለጠውና ምግባራቸው አርአያ የሚሆነውም ለሰላም ሲሉ ለራሳቸው የሚገባውንም ቢሆን አሳልፈው ስለሚሰጡ ነው፡፡ የሌላውን የሚቀሙ ቢሆኑ ኖሮ ሰላማቸው ይወሰድባቸው ነበር፡፡ የብጥብጥና የረብሻ ምክንያትም ይሆኑ ነበር፡፡ ክርስቲያኖች ሲገደሉ የኖሩትም ለምን ሰላማዊ ሆናችሁ? ለምን ዓለምን በፍቅር ለማሻነፍ ተነሣችሁ ተብለው መሆኑን መረዳት ይገባል፡፡

ሰላም የሚያስፈልገው ለክርስቲያኖች ብቻ ሳይሆን እንደ ሀገር ተስማምቶ ለመኖር ጭምር ነው፡፡ በቀላል ነገር ሁሉ የሚከፋን፣ በጥቂት ሆድ የሚብሰን ከሆነ ሰላማችን ይደፈርሳል፡፡ ወጥተን መግባት፣ ተኝተን መነሣት አንችልም፡፡ በአሁኑ ጊዜ ስለ ሰላም ከመናገር ባለፈ ሰላም እንዲመጣ ቁርጥ ውሳኔ መወሰን ተግባራዊ ማድረግ ይኖርብናል፡፡ የሚሰማው ጦርነት፣ ግጭት፣ መለያየት ነው፡፡ እነዚህ ሰላም ካላመጡ ብዙ ወጭ የማይጠይቀውን ሰላምን፣ ፍቅርን፣ ይቅርታን መያዝ ይኖርብናል፡፡

ስጋት፣ ፍራቻ፣ መጠራጠር የሌለበት ይልቁንም ተስፋ፣ ፍቅር፣ እምነት፣ የሚገኝበት ሕይወት የሀገርን ሰላም ጠብቆ ለዜጎች ወጥቶ መግባት ዋስትና ይሰጣል፡፡ ሰላማውያን የሆኑ ክርስቲያኖች እንኳን ከሰው ከአራዊት ጋርም ለመኖር ችለዋል፡፡ ክርስቲያኖች በዚህ ምድር ሲኖሩ ሰላማውያን ናቸው፡፡ ለክርስቶስ ያላቸውን ፍቅር ለመግለጥ ለእነሱ የሚገባውን ሳይቀር አሳልፈው የሚሰጡ፣ ለእኔ ይቅርብኝ ለአንተ ይሁን የሚሉ ናቸው፡፡ ነቢዩ የሚመክረንም ከስግብግብነት ርቀን ያለንን እየሰጠን ሃይማኖታችንን በምግባር እንድንገልጥ ነው፡፡ ከምግባር ዕሴቶች አንዱ ደግሞ ሰላም ነው፡፡ ሰላም የሚመሠረተውም በሆደ ሰፊነት፣ በአርቆ አሳቢነት፣ ስምን ተክሎ ለማለፍና ለትውልድ የሚጠቅም ሥራ ለመሥራት ከመፈለግ ነው፡፡ ዓለምን የለወጡ፣ ለጨለማው ዓለም ብርሃን የሆኑ ሰላማውያን ሰዎች ናቸው፡፡ እንዲህ ዓይነት ሰዎች ተከብረው የሚኖሩ፣ ታሪክ በመልካም ሲያነሣቸው የሚኖሩ መሆናቸውን መረዳት ይገባል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ስለ ሰላም የምትሰብከው ከሰላም ትርፍ እንጂ ኪሳራ፣ ጥቅም እንጂ ጉዳት ስለሌለው ነው፡፡

ሰላም የሚጠፋው እንዴት ነው?

ሰላም በአርቆ አሳቢነትና በይቅርባይነት፥ እንደሚገኝ ሁሉ በተለያዩ ሁኔታዎችና አጋጣሚዎች ሊጠፋ ይችላል፡፡ መላእክት በተፈጠሩ ጊዜ ያልሆነውን ሆኛለሁ፣ ያልፈጠረውን ፈጥሬአለሁ ብሎ በሐሰት በተነሣው በሳጥናኤል ምክንያት በዓለመ መላእክት መካከል ጦርነት እንደተፈጠረ ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዱናል፡፡ ሰላምን የሚያደፍርሱ ወገኖች ለጊዜው ኃይል ያላቸውና የተሳካላቸው ቢመስሉም መጨረሻቸው እንደማያምር ከሳጥናኤል ተምሮ እውነትን፣ ሰላምን፣ ፍቅርን፣ ዕርቅን ገንዘብ ማድረግ ይገባል፡፡ ዓለመ መላእክትን የበጠበጠው ሳጥናኤል እንዳይነሣ ሆኖ የወደቀው መውደቁ አልበቃው ብሎ ሌሎችንም ለመጣል በመፈለጉ ነው፡፡ ሰላምን የሚያጠፉ ወገኖች መጨረሻም እንዲሁ ነው፡፡ አወዳደቃቸው አያምርም እንደ ዲያብሎስ ወደ ታች እየወረዱ ወደ ላይ የሚወጡ ስለሚመስላቸው ከወደቁበት አረንቋ ሳይነሡ ይቀራሉ፡፡

መላእክት ሳጥናኤል በተናገረው ነገር ሳይረበሹ ምንት ንህነ መኑ ፈጠርነ እምኀበ አይቴ መፃዕነ፤ ምንድን ነን? ከየት መጣን? ማን ፈጠረን? ማለት ጀመሩ፡፡ የመላእክትን ጥያቄ ተከትሎ ሳጥናኤል በሐሰት እኔ ፈጠርኳችሁ አለ፡፡ የሳጥናኤን ንግግር ተከትለው ፈጠርከን ያሉም፣ ፈጥረህ አሳየን ያሉም፣ ከሁለቱም ያልሆኑ ወገኖች ነበሩ፡፡ በያለንበት እንጽና የሚለው የቅዱስ ገብርኤል ንግግር ደፍርሶ የነበረውን ሰላም አረጋጋው፡፡ ወዲያውም እምኀበ አልቦ ኀበቦ የፈጠራቸው አምላካቸው ልዑል እግዚአብሔር ተገልጦ ዲያብሎስ ያጠፋውን ሰላማቸውን መለሰላቸው፡፡ የመላእክትን ሰላም ለማደፍረስ የሞከረውን ዲያብሎስም በጨለማ ጠቅልሎ እንጦሮጦስ አውርዶታል፡፡ እኛም በዚህ ዓለም ስንኖር ሰላማችን እንዳይጠፋ መጠንቀቅ ይኖርብናል፡፡ ሰላም ከሚደፈርስባቸው ምክንያቶች ጥቂቶችን ለማቅረብ እንሞክራለን፡፡

  • ለእኔ ብቻ ባይ መሆን፡- የክርስቲያኖች ምግባር የሚገለጠው ከራሳቸው ይልቅ ሌሎችን ማስቀደም በመቻላቸው ነው፡፡ ሀገራችን ተከብራ የምትኖረው በመቻቻል፣ በይቅርባይነትና ሰላማውያን ለመሆን ራሳችንን ስናዘጋጅ ነው፡፡ ለእኔ ብቻ የምንል ከሆነ እንኳን ከሌሎች ጋር ከራሳችንም ጋር ተስማምተን መኖር አንችልም፡፡ ሁልጊዜ ለእኔ ስለምንል ለፍላጎታችን ወሰን ስለማይኖረው ሰላማችን ይታወካል፡፡ ሰላም እንዲሰፍን ሆደ ሰፊ ነገር አላፊ መሆን ይገባል፡፡ ሀገራችን እንደ ሀገር እንድትከብርና እንድትሻሻል ሰላማዊ ዜጎች መሆን፣ ሰላም ሲደፈርስ ለማስተካከል መሞከር ይኖርብናል፡፡ ለዚህ ደግሞ በሃይማኖት የጸና በምግባር የተገራ ትውልድ ያስፈልጋል፡፡ ማኅበረሰብ ሰላሙ ተከብሮ የሚኖረው አርቀው በሚያስቡ፣ ሰላማዊ በሆኑ፣ ለእኛ የሚያስፈልገን ለሌሎችም ያስፈልጋቸዋል በሚሉ ወገኖች ነው፡፡

ሰላም ሲታወክ የሚኖረው ውስጣዊ ሰላማቸውን ባጡ፣ አካላት ነው፡፡ ይህ የሚያሳየው ለራስ ከመጠን ያለፈ ቦታ መስጠትንና ከእኛ በላይ ለሆኑት ቦታ እንዳንሰጥ ለሁሉ ነገር እኔ ብቁ ነኝ ማለትን ያስከትላል፡፡ ይህም ለሰላም መደፍረስ ምክንያት ይሆናል እንጂ ሰላምን ማምጣት አይችልም፡፡ ሰላም የሌላቸው ወገኖች ደጋፊ ሲያገኙ ሰላም እየጠፋ፣ ጉልበት ያላቸው ብቻ የሚፈልጉትን እየፈጸሙ ይኖራሉ፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ድርጊት እንኳን በእግዚአብሔር በሰውም የተጠላ ነው፡፡ እንዲህ የሚያደርጉትም ዘራቸው በአንድ ትውልድ ተደምስሶ መቀጣጫ ሆነዋል፡፡

ሰላም የሚገኘው ግን ለእኔ ብቻ በማለት ሳይሆን በትሕትናና በይቅርባይነት ነው፡፡ ለእኔ ብቻ ማለትም ልዩነትን እንጂ ሰላም አያመጣም፡፡ ለዘመናችን የሚያስፈልገው መደማመጥ፣ መከባበር፣ ለእኔ የሚያስፈልገኝ ለሌላውም ያስፈልገዋል ብሎ ማሰብና ያሰቡትን በተግባር መግለጥ ነው፡፡

ያልፈጠረውን ፈጥሬያለሁ ያለው ዲያብሎስ የመላእክትን ሰላም በማደፍረስ እንዳልቆመ ለእኔ ብቻ ባዮችም የብዙዎችን ሰላም ያደፈርሳሉ፡፡ ዲያብሎስ የወደቀው ለእግዚአብሔር የሚገባውን ለእኔ ይገባል በማለቱ ነው፡፡ በጎደለው ነገር በእሱ ምትክ የተፈጠረውን የሰውን ልጅ ማወኩን ቀጠለ፡፡ የሰው ልጅ ይኖርባት ዘንድ በተሰጠችው በገነት እያመሰገነ እንዳይኖር የፈጠረውን እግዚአብሔርን እንዳይከተል ዲያብሎስ ለእርሱ የማይገባውን መልካም አስመስሎ በማሳየት አታለለው፡፡ የማይገባንን መሻትና ለእኔ ማለት በዓለም ላይ ጦርነት እንዲነግሥና ሰላም እንዲታጣ ሲያደርግ ኖሯል፡፡ ይህ የማያዋጣ በመሆኑና ከእግዚአብሔርም ስለሚለየን ሰላማዊ ለመሆን መዘጋጀት ይኖርብናል፡፡

  • ለክፉዎች ደጋፊ መሆን፡- ሰዎች ባለማወቅ ወይም በየዋህነት ለክፉዎች ደጋፊ ይሆናሉ፡፡ በዚህም ሌሎችንም ራሳቸውንም ይጎዳሉ፡፡ የሰው ልጅ በዲያብሎስ ምክር ተታልሎ የነበረውን ክብር አጥቶ አምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን ያለ ሰላም፣ ያለ ዕረፍት ኖሯል፡፡ እግዚአብሔርን ያህል ጌታ ገነትን ያህል ቦታ አጥቷል፡፡ በርደተ መቃብር ላይ ርዕደተ ገሃነም ተፈርዶበታል፡፡ ለክፉዎች ሰዎች ደጋፊ ስንሆንም ሰላማችንን ከማጣት በተጨማሪ ሕይወታችንንም እናጣለን፡፡ በምድር ላይ ዕድሜያችን እንዲረዝምና ከስጋት ለመዳን ሰላማችንን ከሚያደፈርሱብን፣ ከእግዚአብሔር ከሚለዩን መራቅ ይኖርብናል፡፡ የተቀደሰውን ቃል ለግል ዓላማ ማስፈጸሚያ ከሚያደርጉ ወገኖች መራቅ ይገባል፡፡ ኃጢአት ከሚያሳስቡን መሸሽ ሰላማችን ተጠብቆ እንዲኖር ያደርጋል፡፡ የራሳቸውን ድብቅ ዓላማ ለማሳካት የሚፈልጉ ወገኖች አርቀው የማያስቡ አካላትን ጥግ አድርገው ፍላጎታቸውን ያሳካሉ፡፡ መረዳት የሚገባው ግን በእንዲህ ዓይነት መንገድ ሰላም የማይገኝ መሆኑን ነው፡፡
  • ትዕግሥት በማጣት፡- ትዕግሥት የሁሉ ነገር መሠረት ነው፡፡ ትዕግሥት ተደማምጦ ሥራ ለመሥራት አሳብ ለመለዋወጥ፣ የሚገጥምን ፈተናን ድል ለማድረግ ይጠቅማል፡፡ ቅዱሳን የእግዚአብሔርን መንግሥት የወረሱት በትዕግሥት ነው፡፡ የሚገጥማቸውን ፈተና ይዋል፣ ይደር በማለት ያሸንፉታል፡፡ ቀስ በቀስም እግዚአብሔር ፈተናውን የሚታገሡበትን፣ ለድል አክሊል የሚበቁበትን ጥበብ ይገልጥላቸዋል፡፡ ፈተናን ድል ማድረግ የሚያስገኘውን በቊዔት ስለሚረዱም እግዚአብሔርን እየጠየቁ፣ ታላላቆቻቸውን እያማከሩ በሚገጥማቸው ፈተና ላይ ይሠለጥኑበታል፡፡ በትዕግሥታችሁ የእግዚአብሔርን መንግሥት ትወርሳላችሁ ተባልን እንጂ በችኮላና በስሜታዊነት ትወርሳላችሁ አልተባልንም፡፡ የታዘዝነው መከራ ሲገጥመን መታገሥና ሰው በሌለበት ጊዜ ሰው ሆኖ መገኘት መሆኑን “ወንድሞች ሆይ ልዩ ልዩ መከራ በሚመጣባችሁ ጊዜ በሁሉ ደስ ይበላችሁ፡፡ በሃይማኖታችሁ የሚመጣባችሁ ፈተና ትዕግሥትን እንደሚያደርግላችሁ ዐውቃችሁ ምንም የሚጎድላችሁ ሳይኖር ፍጹማንና ጤነኞች ትሆኑ ዘንድ ትዕግሥት ፍጹም ግብር አላት” (ያዕ. ፩፥፪፬) የሚለውን የሐዋርያውን ትምህርት መረዳት ይገባል፡፡

ከሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ይልቅ ሥርዓተ ሰብእን፣ ከትዕግሥት ይልቅ ስሜታዊ መሆንን ስንመርጥ በእግዚአብሔር ሕግ ከመመራት ይልቅ ስሜታዊነት ይቆጣጠረናል፡፡ ፍትሕንም በራሳችን ለማግኘት፣ የፈለግነውን ለመወሰንና ለመፈጸም እንነሣሣለን፡፡ ይህ ደግሞ ከእግዚአብሔር ያርቀናል፡፡ በስሜታዊነትና ትዕግሥት በማጣት የፈጸምነው ጥፋት ለጸጸትና ለሕሊና ወቀሳ ይዳርገናል፡፡ ሰው ስናይ የምንበረግግ፣ ኮሽ የሚል ነገር ሁሉ የሚያስደነግጠን እንሆናለን፡፡ እንዲህ ላለመሆን ትዕግሥትን ገንዘብ ማድረግ ለራሳችንም፣ ለቤተሰቦቻችንም፣ ለሀገራችንም ይጠቅማል፡፡ ሐዋርያው የሚመክረንም “በትሕትና ሁሉና በየዋህነት፣ በትዕግሥትም እርስ በራሳችሁ በፍቅር ታገሡ፣ በሰላም ማሰሪያ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ትጉ (ኤፌ. ፬፥፪-፫) በማለት በመሆኑ ምክሩን በተግባር ለመፈጸም መትጋት ይኖርብናል፡፡ ሐዋርያው ከእግዚአብሔር ከሚያርቁንና ሰላማችንን ከሚነጥቁን እንድንርቅ ከመከረን በኋላ መከተል የሚገባንን ደግሞ “አንተ ግን የእግዚአብሔር ሰው ሆይ ከዚህ ሽሽ ጽድቅንና እግዚአብሔርን መምሰል፣ እምነትንም፣ ፍቅርንም፣ መጽናትንም፣ የዋህነትንም ተከተል፡፡ መልካሙን የእምነት ገድል ተጋደል፤ የተጠራህበትንም በብዙ ምስክሮች ፊት በመልካም መታመን የታመንህለትን፣ የዘለዓለምን ሕይወት ያዝ (፩ኛ ጢሞ. ፮፥፲፩-፲፫) በማለት ይመክረናል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም “መከራን የሚታገሥ ሰው ብፁዕ ነው፤ ተፈትኖ እግዚአብሔር ለሚወዱት ተስፋ ያደረገላቸውን የሕይወት አክሊል ይቀበላልና” (ያዕ. ፩፥፲፪) በማለት እንድንጸና ያሳስበናል፡፡ሰላም የሚደፈርሰው ከላይ በዘረዘርናቸውና በሌሎችም መሰል ምክንያቶች ነው፡፡ እነዚህ መጥፎ ተግባራት ለራስም፣ ለቤተሰብም አይጠቅሙም፡፡ ቤተሰብን ይበትናሉ፤ ሀገርንም ያፈርሳሉ፡፡ ለዚህ ነው ነቢዩ ሰላምን ገንዘብ በማድረግ ሰላማዊ ሆነን እንድንኖር የሚመክረን፡፡

  • ሰላም እንዴት ይገኛል?
  • ለሌሎች ቅድስሚያ በመስጠት፡- ሰላም ከሚገኝባቸው መንገዶች አንዱ ራስን ከስግብግብነት በመጠበቅ ለሌሎች ቅድሚያ በመስጠት ነው፡፡ ለሌሎች ቅድሚያ ስንሰጥ ለመጣላት ተዘጋጅተው የነበሩት ስሜታቸው ይቀዘቅዝና በድርጊታቸው ያፍራሉ፡፡ ቆይተውም ራሳቸውን ይወቅሳሉ፡፡ በሌላ በኩል የራሳቸውን ታናሽነት ቅድሚያ የሰጣቸውን አካል ታላቅነት ይቀበላሉ፡፡ ቀስ በቀስም እነሱም መልካም ወደማድረግና ተቀብለው ከመደሰት ሰጥተው ወደ መደሰት ይሸጋገራሉ፡፡ ቅድሚያ ለእኔ የሚሉ ወገኖች ልዩነትን እንደሚፈጥሩና ሰላምን እንደሚያደፈርሱ ሁሉ እኔ ይቅርብኝ ቅድሚያ ለእናንተ የሚሉ ደግሞ ሰላምን ያመጣሉ፡፡ የክርስቲያኖች መርሕም ይህ ነው፡፡ ለእነሱ የሚያስፈልገውን ለሌላው ይሰጣሉ፡፡

ለእስራኤል ርስትን ያወረሰው ኢያሱ የወሰደው የማይረባውን ሲሆን ለሌሎች ያከፋፈለው ግን ምርታማውንና ለም የሆነውን መሬት ነው፡፡ ኢያሱ ይህን ቢያደርግም እግዚአብሔር ደግሞ በበረከት ጎብኝቶት ከማይረባው ቦታ ለራሱና ለወገኖቹ የሚበቃ ምርት ሲሰበስብ ኖሯል፡፡ ከዚህም በመንገብገብ የምናተርፈው፣ ለሌሎች በመስጠትም የሚጎድልብን አለመኖሩን እንረዳለን፡፡ ከእግዚአብሔር ይሰጣችኋል የተባሉት ሁሉን ለእኔ የሚሉት ሳይሆኑ ይህስ ለወገኔ ይገባል የሚሉት እንደሆኑ መጻሕፍት ያስተምሩናል፡፡ ቅድሚያ ለእኔ በማለታችን በሰው ፊት ከመናቃችንም በተጨማሪ ሕሊናችንም ሰላም አይሰጠንም፡፡ ሕሊናችንን ሰላም የማይሰጠውን ተግባር ከመፈጸም ይልቅ ሌሎችን በማስቀደም ሕሊናችንን የሚያስደስት ተግባር መፈጸም ይገባል፡፡ በየሔድንበት የሰው መጠቋቆሚያ የሕሊና ወቀሳ ከምናተርፍ የሰላም እንቅልፍ ተኝተን የምናድርበትን ሥራ መሥራት ለራሳችንም ለሀገራችንም ይጠቅማል፡፡ ይህም ማለት የምንሠራውን እንወቅ ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ “ስለዚህ እንደ ቸርነቱ የሰጠን ይህ መልእክት አለንና አንሰላችም፡፡ ነገር ግን በስውር የሚሠራውን አሳፋሪ ሥራ እንተወው፤ በተንኰልም አንመላለስ፤ የእግዚአብሔርንም ቃል በውሸት አንቀላቅል፤ ለሰውም ሁሉ አርአያ ስለመሆን እውነትን ገልጠን በእግዚአብሔር ፊት ራሳችንን እናጽና” (፪ኛ ቆሮ. ፬፥፩-፪) በማለት እንደመከረን ልብ እንበል፡፡

  • ትዕግሥትን ገንዘብ ማድረግ፡- የእግዚአብሔር ሰዎች ተብለው የተመሰገኑት ስሜታቸውን ተቈጣጥረው፣ ፈቃደ ሥጋቸውን ለፈቃደ ነፍሳቸው ያስገዙት ናቸው፡፡ እንዲህ የሚያደርጉ ወገኖች እንኳን ከሰው ከአራዊት ጋር ተስማምተው ይኖራሉ፡፡ ስሜታቸው የጠየቃቸውን ሁሉ ለማግኘት የፈለጉ፣ ለፈቃደ ሥጋቸው አርነት የሰጡ ወገኖች መጨረሻቸው አላማረም፡፡ በአንጻሩ ትዕግሥትን ገንዘብ ያደረጉት ግን በሰውም በእግዚአብሔርም ፊት ተመስግነዋል፡፡ እነዚህ ወገኖች በፈቃደ ሥጋቸው ላይ የሠለጠኑ በመሆናቸው በቀላሉ ከሰዎች ጋር ግጭት ውስጥ አይገቡም፡፡ እንዲህ ተደረጋችሁ ቢባሉም በስሜት ተገፋፍተው ወደ መጣላት አይሔዱም፡፡

በጾም ወቅት ብሉ፣ ብሉ የሚል ስሜት ሲመጣባቸው ትንሽ ልቆይ እያሉ ረሃብን ድል ይነሡታል፡፡ ፈቃደ ሥጋቸው ተነሣሥቶ ወደ ዝሙት የሚገፋ ፈተና ሲገጥማቸውም እግዚአብሔርን በጸሎት በመማጸን ከመምህራን ምክርን በመጠየቅ ፈተናውን ያልፉታል፡፡ ከዚያ በኋላ ፈቃደ ዝሙት ይጠፋላቸዋል፡፡ ያየውን ሁሉ ለእኔ የሚል ስሜት ሲመጣም በትዕግሥት ድል ነሥተው ራሳቸው ከጸጸት ተጠብቀው እግዚአብሔርንም ያስደስታሉ፡፡ ለተከታዮቻቸውም አርአያ ይሆናሉ፡፡ በአጠቃላይ ከክርስቲያኖች የሚጠበቀው የመንፈስ ፍሬዎችን በመፈጸም ጽድቅን ገንዘብ ማድረግ ነው፡፡ ሐዋርያው “የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር፣ ደስታ፣ ሰላም፣ ትዕግሥት፣ ምጽዋት፣ ቸርነት፣ እምነት፣ ገርነት፣ ንጽሕና ናቸው፡፡ ከዚህ ሕግ የሚበልጥ የለም፡፡ በኢየሱስ ክርስቶስ የሚያምኑ ግን ሰውነታቸውን ከምኞትና ከኃጢአት ለዩ፡፡ አሁንም በመንፈስ እንኑር በመንፈስም እንመላለስ፡፡ ኩሩዎች አሁንም እርስ በርሳችንም አንተማማ፤ እርስ በርሳችንም አንቀናና” (ገላ. ፭፥፳፪-፳፮) በማለት እንዳስተማረን፡፡

ትዕግሥት በሃይማኖት ሰዎች፣ በመሪዎች፣ ለሀገር በሚያስቡ ሰዎች ውስጥ ካልተገኘች ተቻችሎ መኖር አይቻልም፡፡ ትዕግሥት የፈለጉትን የምታሰጠው በእርጋታ ለማሰብ መሠረት በመሆኗ ነው፡፡ ክርስቲያኖች መንግሥተ ሰማያትን ይወርሳሉ የተባሉት በትዕግሥት ነው፡፡ ከትዕግሥት ትርፍ እንጂ ኪሳራ ስለሌለው በሰላም ለመኖር ትዕግሥትን ገንዘብ ማድረግ ይገባል፡፡

  • ዕርቅ፡- ሰላም ለማምጣት መሠረት የሆነው ዕርቅ ነው፡፡ “የሚያስታርቁ ብፁዓን ናቸው የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉና” (ማቴ. ፭፥፱) የተባለው ዕርቅ በዚህ ዓለም በሰላም ለመኖር በወዲያኛው ዓለም መንግሥተ ሰማያትን ለማውረስ ወሳኝ በመሆኑ ነው፡፡ ዕርቅ ማድረግ የሚጀምረው ከራስ ነው፡፡ ከራስ ጋር ዕርቅ የፈጸመ ሰው ከሌላው ጋር ታርቆ በሰላም ለመኖር ይችላልና፡፡ ዕርቅን የፈጸመ ሰው ክፋትን ይጸየፋል፡፡ ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ “እንግዲህ ክፋትንም ሁሉ፣ ሐሰት መናገርንም ሁሉ፣ ጥርጥርንም መተማማትን፣ መቃናትንም ከእናንተ አርቁ፡፡ ዛሬ እንደተወለዱ ሕፃናትም ሁኑ፤ ለመዳን በእሱ ታድጉ ዘንድ ቅልቅል የሌለባትን የቃልን ወተት ተመኙ” (፩ኛ ጴጥ. ፪፥፩-፫) በማለት ያስተማረውን መረዳት ይገባል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም አርቆ ማሰብ፣ የምንፈጽመው ነገር የሚያስከትለውን በጎም ሆነ መጥፎ ተጽዕኖ መመዘን ዕርቅ ለማድረግ ይጠቅማል፡፡ ከራሱም ከእግዚአብሔርም ጋር ተጣልቶ ሲቅበዘበዝ ከኖረው ከቃየን ሕይወት መለየት በሰላም ለመኖር ያስችላልና ሰላምን የሚያሰፍን ሥራ ለመሥራት እንዘጋጅ፡፡

ምንጭሰምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 26ኛ ዓመት ቁጥር 1 ቅጽ 26ቁጥር 394 ከመስከረም 16-30ቀን 2011ዓ.ም

“ሰላምን ሻት ተከተላትም”(መዝ.፴፫፥፲፬)

በመ/ር ኃይለ ሚካኤል ብርሃኑ
ሰላም ማለት ጸጥታ፣ ዕረፍት፣ እርጋታ፣ እርካታ ማለት ሲሆን የእርስ በእርስ ስምምነት በአንድነት አብሮ መኖር መቻልና የዕረፍት ስሜት እንደሆነ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ያስረዳል፡፡ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “ሰላምን ሻት ተከተላትም” ብሎ ከመናገሩ አስቀድሞ የመጽሐፉን ክፍል ወደ ኋላ መለስ ብለን የተነሳንበትን ኃይለ ቃል ሙሉ አሳቡን ለመረዳት ስንመለከተው እንዲህ የሚል ቃል እናገኛለን፡፡ “ልጆቼ ኑ ስሙኝ እግዚአብሔርን መፍራት አስተምራችሁ ዘንድ፤ ሕይወትን የሚፈቅድ ሰው ማን ነው? በጎ ዘመንንም ለማየት የሚወድድ ማን ነው? አንደበትህን ከክፉ ከልክል ከንፈሮችህም ሸንገላን እንዳይናገሩ ከክፉ ሽሽ መልካንም አድርግ ሰላምን ሻት ተከተላትም” ይላል፡፡
ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት ሰላምን የምንሻበትን ምክንያት በዚሁ በተመለከትነው ኃይለ ቃል ላይ ገልጦታል፡፡ እንደ አባትነቱ እግዚአብሔር ልጆቹ ለምንሆን ለእኛ ሊያስተምረን የፈቀደለትንና እርሱ በሕይወቱ ገንዘብ አድርጎት በእግዚአብሔር እንደ ልቤ ተብሎ የተመረጠበትን ጥበብ ለእኛም ሲያካፍለን “እግዚአብሔርን መፍራት አስተምራችኋለሁአለ፡፡ምክንያቱም እግዚአብሔርን መፍራት ከሁሉ ይልቅ ቀዳሚ ነውና፡፡ ለዚህም ነው አባትና ልጅ ተባብረው(ተቀባብለው) የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት እንደሆነ የነገሩን(መዝ. 111፥10፣ምሳ.1፥7፣9፥10)፡፡
ከሁሉ አስቀድሞ በሕይወታችን እግዚአብሔርን መፍራት ትርጉም ላለው ሕይወት አስፈላጊ ነው፡፡ ሰላምን የምንሻበት መንገድ እሱ ነውና፡፡ ቅዱስ ዳዊት እግዚአብሔርን መፍራት ሕይወትን የሚያስገኝና በጎ ዘመንን ለማየት የምንችልበት የጥበብ (የዕውቀት) ሁሉ መሠረት ነው፡፡ ይህንንም ከገለጸ በኋላ “ሕይወትን የሚፈቅድ ሰው ማን ነው? በጎ ዘመንንም ለማየት የሚወድድ ማን ነው? ብሏል፡፡ ከላይ እንዳየነው ሕይወትን ለማግኘት የሚሻ በጎ ዘመንንም ለማየት የሚፈልግ ጥበብን (ማስተዋልን) ገንዘብ ያደረገ ሰው ነው፡፡ በመሆኑም ሕይወትን ለማግኘትና በጎ ዘመንን ለማየት የሚሻ ሰው ምን ማድረግ እንዳለበት ስንመለከትም ቅዱስ ዳዊት እንደነገረን ቀጥለን በዝርዝር እንመለከታቸዋለን፡፡
      ፩ኛ አንደበትን ከክፉ መከልከል
የሰው ልጅ በልቡ ያሰበውን በአንደበቱ ይናገራል፡፡ በልብ የታሰበውን መልካምም ይሁን ክፉ የሚያውቀው እግዚአብሔር ብቻ ሲሆን ነገር ግን የታሰበው ነገር በውጫዊ ሰውነት ላይ በሚታዩ ምልክቶች (ገጽን በማየት) መታወቅ የሚችልበት አጋጣሚ ከተፈጠረ ወይም በአንደበት ቢነገርና በሥራ ቢተገበር ሰዎች ይረዱት ይሆናል፡፡
ይሁንና አንደበትን ከክፉ ካልከለከሉት ሰዎችን የሚጎዳና የማይሽር ጠባሳ ጥሎ የማለፍ በዚያም ሰበብ ተናጋሪውን ሳይቀር ሁለተኛውን አካል በቁጣ በመጋበዝ ለሞት የማብቃት ዕድል አለው፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ያዕቆብ በመልእክቱ “ምላስ እሳት ናት እነሆ ትንሽ ምላስ በሰውነታችን ውስጥ ዐመፅ የተመላበት ዓለም ናት ሥጋችንን ትበላዋለች ውስጣዊ ሰውነታችንንም ትጠብሰዋለች ከገሃነምም ይልቅ ታቃጥላለች” ይላል፡፡
ስለዚህ ሕይወትን የሚፈቅድና በጎ ዘመንን ለማየት የሚፈልግ ሰው አንደበቱን ከክፉ ነገር መከልከልና መጠበቅ ያስፈልጋል፡፡ ተናግሮ ሰውን ላለማስቀየምና ላለማስከፋት መጠንቀቅ አለበት፡፡ ሌላውንም ሰው ወደ ጥፋት ላለመምራት ማስተዋል ተገቢ ነው፡፡ አንደበት ኃያል ነውና ጦር ከፈታው ወሬ የፈታው ይበልጣል የሚል አባባል እንዳለ እናስታውሳለን፡፡
አንደበትን ከክፉ ካልከለከልነው ስድብንና ሐሜትን እናበዛለን፡፡ ይህ ደግሞ ከሕይወት ጎዳና የሚያወጣ ክፉ ተግባር ነው፡፡ በጓደኛ መካከል፣ በባልና ሚስት መካከል፣ በአንድ ሀገርና በሌላው ሀገር መካከል፣በጎሳና በጎሳ መካከል ፣ በጎረቤትና በጎረቤት መካከል ሐሜትና መነቃቀፍ፣ ስድብና ጥላቻ ካለ በጎ ዘመንን ማየት አይቻልም፡፡ ነገር ግን ሕይወትንም ሆነ በጎ ዘመንን ለማየት አንደበትን ከክፉ መከልከልና በጎ ነገርን ማውራት አስፈላጊ ነው፡፡
                                                           ፪ኛ. ከክፉ መሸሽ
ከክፉ መሸሽ ማለት ክፉን ከማድረግ መቆጠብና ክፉ ከሚያደርጉት ጋር በክፋታቸው አለመተባበር ነው፡፡ የእግዚአብሔር ሰው ሁል ጊዜም ቢሆን ከክፉዎች ጋር ኅብረት የለውም አባታችን ያዕቆብ ልጆቹን በሚመርቅበት ጊዜ ክፉ ሥራ ከሠሩ ከልጆቹ የክፋት ሥራ ጋር እንደማይተባበርና ከክፋት ጋር ኅብረት እንደሌለው ገልጧል፡፡ “ስምዖንና ሌዊ ወንድማማቾች ናቸው፡፡ በጭቅጭቃቸውና በጦራቸው ዐመጽን ፈጸሟት በምክራቸው ሰውነቴ አትገናኛቸው አሳቤም በአመጻቸው አትተባበርም በቊጣቸው ሰውን ገድለዋልና በገዛ ፈቃዳቸውም የሀገርን ሥር ቆርጠዋልና ቁጣቸው ርጉም ይሁን ጽኑ ነገርና ኩርፋታቸውም ብርቱ ነበርና በያዕቆብ እከፋፍላቸዋለሁ በእስራኤልም እበታትናቸዋለሁ” (ዘፍ.49፥5)
ያዕቆብ ምንም እንኳ በሥጋ የወለዳቸው ልጆቹ ቢሆንም በፈጸሙት ክፉ ሥራ ግን እንደማይተባበር ከክፉ ሥራቸው የራቀና ከክፋት የተለየ መልካም አሳብ እንዳለው ገልጧል፡፡ ዛሬም ቢሆን የሰው ልጆች ክፋትና በደል እየበዛ ባለበት ሰዓት የእግዚአብሔር ልጆች ከክፋት፣ ከተንኮል፣ ከውሸት፣ ከሌብነት፣ ከቅሚያ፣ ከዝርፊያ፣ ከጭካኔ፣ ከሴሰኝነት፣ ከዘማዊነት፣ ከዘረኝነት በአጠቃላይ ለራስም ለሀገርም ከማይበጁ እኩይ ምግባራትና ከሚፈጽሟቸው ሰዎች ጋር መተባበር የለብንም፡፡ ቅዱስ ዳዊት እንደነገረን ሕይወትን ለማግኘት የምንሻና በጎ ዘመን ለማየት የምንፈልግ ሁሉ ከክፉዎች ጉባኤ መለየትና አለመተባበር ያስፈልጋል፡፡
                                                     ፫ኛ. መልካም ማድረግ
ሕይወትን ለማግኘትና በጎንም ዘመን ለማየት የሚሻ ሰው ሁሉ መልካምን ሁሉ ሊያደርግ ያስፈልገዋል፡፡ ከክፉ መሸሻችንና ከከፉዎች ጋር አለመተባበራችን መልካም ሥራ ለመሥራት መሆን አለበት እንጂ ከሥራ ርቀን እንዲሁ እንድንኖር አይደለም፡፡ያለ በጎ ሥራ መኖር ስንፍና ነውና፡፡
እግዚአብሔር የሰውን ውድቀቱንና መጥፋቱን የማይሻ አምላክ ስለ ሆነ በማወቅም ይሁን ባለማወቅ በክፉ ሥራ ተጠምዶ የነበረ ሁሉ ሊመለስና በሕይወት ሊኖር ይገባዋል፡፡ በቀደመው ስሕተቱ ወንድሙን ያሳዘነ፣ሰው የገደለ፣አካል ያጎደለ፣ ግፍን የፈጸመ፣የድሃውን ገንዘብ በተለያየ ሰበብ የዘረፈ፣ጉቦ የተቀበለ፣በነዚህና መሰል እኩይ ሥራዎች ሀገሩን የጎዳ፣ እግዚአብሔርን የበደለ ሁሉ ከልብ በመጸጸት በልቅሶና በዋይታ ወደ እገዚአብሔር መመለስ ያስፈልገዋል፡፡ ለዚህም አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር በነቢዩ ሕዝቅኤል ላይ አድሮ ኃጢአተኛው ከኃጢአቱ ተመልሶ በሕይወት መኖር እንዳለበት አስገንዝቦናል፡፡
“እኔ ሕያው ነኝና ኃጢአተኛው ከመንገዱ ተመልሶ በሕይወት ይኖር ዘንድ እንጂ ኃጢአተኛው (በደለኛው) ይሞት ዘንድ አልፈቅድም ይላል ጌታ እግዚአብሔር፡፡የእስራኤል ቤት ሆይ ተመለሱ ከከፉ መንገዳችሁ ተመለሱ ስለምንስ ትሞታላችሁ? (ሕዝ.33፥11) እንዲል፡፡
እግዚአብሔር በነቢዩ ላይ አድሮ እንደ ነገረን በደለኛ ሰው በበደሉ ቀጥሎ መጥፋት የለበትም፡፡መመለስና በሕይወት መኖር ያስፈልገዋል እንጂ፡፡ እሱም እንደ በደሉ ዓይነት የቅርታ ጠይቆ፣ ንስሓ ገብቶ፣ የበደለውን ክሶ፣ የሰረቀውን መልሶ፣ የሰበረውን ጠግኖ፣ ያጎደለውን መልቶ በፍጹም መጸጸት ሊመለስና መልካም በመሥራት ሌት ተቀን ከሚተጉት ጋራ በመልካም ሥራ ሊተባበር ያስፈልገዋል፡፡
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረን “ስለዚህ ሐሰትን ተውአት ሁላችሁም ከመንገዳችሁ ጋር እውነትን ተነጋገሩ እኛ አንድ አካል ነንና አትቆጡ አትበድሉም ፀሐይ ሳይጠልቅም ቊጣችሁን አብርዱ ለሰይጣንም መንገድን አትስጡት የሚሰርቅም እንግዲህ አይስረቅ ነገር ግን ድሃውን ይረዳ ዘንድ በእጆቹ መልካም እየሠራ ይድከም” (ኤፌ. 4፥25) ይላል፡፡
                                                                           ሰላምን መሻት 
ሰላም ለሁሉ ነገር አስፈላጊና ሁሉን ለማድረግ የምንችልበት የመልካም ነገር ሁሉ በር ነው፡፡ ሰላምን መፈለግ ሕይወትን ለማግኘትና በጎ ዘመንንም ለማየት ያስችላል፡፡ በአይነቱ ሰላምን በሁለት መልኩ እናየዋለን፡፡ እሱም የውስጥ ሰላምና የውጭ ሰላም ወይም ውስጣዊ ሰላምና ውጫዊ ሰላም ብለን እንመድበዋለን፡፡
የሰው ልጅ ለመኖር ውስጣዊ ሰላምም ሆነ ውጫዊ ሰላም ያስፈልጉታል፡፡ ውስጣዊ ሰላም የምንለው አንድ ሰው ከፍርሐት፣ ከጭንቀት፣ ከመረበሽ፣ ከሥጋትና ወዘተ ነጻ ሆኖ መኖር ሲችል ውስጣዊ ሰላም አለው ይባላል፡፡ ይህም የውስጥን ሰላም ከሚያደፈርሱ፣ አእምሮን ከሚረብሹ፣ ልብን ከሚያቆስሉ፣ የጸጸት እሮሮን ከሚያስከትሉ ነገሮች ስንርቅና ለአእምሮ የሚመች ሥራ ስንሠራ ውስጣችን ሰላም ይሆናል፡፡ውጫዊ ሰላም የምንለው ደግሞ፡- ከቤተሰብ፣ ከጓደኛ፣ ከጎረቤት፣ ከሀገራት ጋር ተስማምተንና ተግባብተን ተቻችለንና ተረዳድተን በፍቅር ተሳስረን መኖር ነው፡፡ በመሆኑም ሰላም ከጥል፣ ከመለያየት፣ ከመጠላላት፣ ከመገፋፋት፣ ከመነቃቀፍ ተቆጥበን የጠብንና የጦርነትን ወሬ ባለመስማትና በስምምነት ተግባብቶ በመኖር የሚገለጥ ነው፡፡ ስለዚህ ሰላም ለሁሉ እንደሚያስፈልገው ካወቅን የሰላም መገኛ ማን እንደሆነና ሰላም ከየት እንደሚገኝ ማወቅ ደግሞ አስፈላጊ ነው፡፡

                                                                         የሰላም መገኛ
ሰላም የሚገኘው የሰላም ባለቤት ከሆነው ከልዑል እግዚአብሔር ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ እንደገለጠው እውነተኛ ሰላም ከእግዚአብሔር ይገኛል፡፡ እርሱ የሰላም አምላክ ነውና (ሮሜ. 15፥33)፡፡ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰላም አለቃ ተብሏል፡፡ “ሕፃን ተወዶልናልና ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል ስሙም ድንቅ መካር፣ ኃያል አምላክ፣ የዘለዓለም አባት፣ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል” (ኢሳ. 9፥6) እንዲል፡፡
ዓለም ለአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን ያህል ሰላሙን አጥቶ በመቅበዝበዝ ይኖር የነበረ ሲሆን በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሰው መሆን፣ መሞትና መነሣት እውነተኛውን ሰላም አግኝቷል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእርሱ ሞት ምክንያት ፍርሐት ጸንቶባቸው ለነበሩት ደቀ መዛሙርት “ሰላምን እተውላችኋለሁ ሰላሜንም እሰጣችኋለሁ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጠው አይደለም ልባችሁ አይደንግጥ አትፍሩም (ዮሐ.14፥27) በማለት ፍርሐትን፣ ስጋትን፣ ጭንቀትን፣ ሁከትን፣ መረበሽን የሚያርቀውን (የሚያስወግደውን) እውነተኛውን ሰላም አደለን፡፡
ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት እንዳለው ሕይወትን ለማግኘትና በጎ ዘመንን ለማየት የምንሻ ሁሉ ሰላምን መሻት ያስፈልጋል፡፡ ደግሞም ሰላምን መሻት ብቻ ሳይሆን መከተል ተገቢ ነው፡፡ ምክንያቱም መሻት ብቻውን ዋጋ ሊኖረው ስለማይችል፡፡ መሻታችን ወደ ማግኘት የሚደርሰው የምንሻውን ነገር ለማግኘት ወደ መገኛው መጓዝና መቅረብ ሲቻል ነው፡፡ ለዚህም ነው ሰላምን ሻት ካለ በኋላ ተከታላትም በማለት በሰላም መንገድ መጓዝ፣ የሰላም ወሬ ማውራት፣ ለሰላም የሚስማማ ሥራ መሥራት የራሳችን ሰላም መጠበቅና የሌላውንም ሰላም አለማደፍረስ ማለት እንደሆነ የነገረን፡፡በሀገራችን ኢትዮጵያ በአሁኑ ሰዓት እየተሰማ ያለው የሰላም ዜና፣እየዘነበ ያለው ሰላም ፣እየተጠረገ ያለው የሰላም መንገድ ለዚሁ ማሳያ ነው፡፡ በአንድም ይሁን በሌላ ምክንያት ተራርቀው የነበሩ ሁለት አካላት የሚያለያያቸውን የጥላቻ ድንበር አፍርሰው የሚያገናኛቸውን የፍቅር ድልድይ መመሥረት አንዱ የሰላም መንገድ የሰላም መገለጫ ነው፡፡
ወደ ቤተ ክርስቲያን አባቶችም ስንመጣ ቀደም ሲል በነበሩት ዓመታት ተለያይቶ የነበረው ቅዱስ ሲኖዶስ ልዩነቱን እንደ ውበት ቆጥሮ ወደ መቀራረብና ወደ አንድነት ጉባኤ ለመምጣት የዘረጋው የሰላም መድረክ አንዱ የሰላም መገለጫ ነው፡፡ስለዚህ እንደ ግል ከራስ ጋር ተስማምቶ፣እንደ ሀገር በሀገር ውስጥ ካሉት ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ጋር ተግባብቶ መኖር የሚያስችሉትን የፍቅር መረቦች መዘርጋት የሰላም መንገድ፣ ሰላምን መሻትና መከተል ነው፡፡
የእግዚአብሔር ሰላም ለሁላችን ይሁንልን፡፡ አሜን
ምንጭ፤ሐመር መጽሔት 26ኛ ዓመት ቁጥር 3 ሐምሌ 2010ዓ.ም

  የ፳፻፲፩ ዓ.ም የአጽዋማት ባሕረ ሐሳባዊ ቀመር

በዲ/ን ታደለ ሲሳይ

በዘመናት ሁሉ የነበረው ያለውና የሚኖረው፣ ሁሉን የፈጠረ በሁሉም ያለ እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ ለእርሱ በዚህን ጊዜ መኖር ጀመረ፣ በዚህን ጊዜ መኖር ያቆማል የማይባልለት የህልውናው መጀመሪያም ሆነ መጨረሻ የሌለው ዘለዓለማዊ ነው፡ “ተራሮች ሳይወለዱ ምድርም ዓለምም ሳይሠሩ ከዘላለም እስከ ዘለዓለም ድረስ አንተ ነህ”፡፡ “ኢየሱስም እውነት እውነት እላችኋለሁ አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ አላቸው፡፡”፣ ብሏል፡፡ በተጨማሪም፣ “ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትናና ዛሬ እስከ ዘለዓለም የሚኖር እርሱ ነውና” እንዲል /መዝ.89÷2፣ዮሐ. 8÷56-69 ዕብ.13÷8/፡፡

የሰው ልጅ ሐሳቡ፣ ንግግሩና ተግባሩ የሚከናወነው በጊዜ ነው፡፡ የጊዜያትና የዘመናት ቁጥርም ከሰው ልጅ ሕይወት ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ የጊዜያትና የዘመናት ቁጥርም ከሰው ልጅ ሕይወት ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ ዘመን ማለት በኅሊና ሲመረመር የጊዜና የዕድሜን መጠንና ልክ የሚወስን መሆኑን መጽሐፈአቡሻኸር ያስረዳል፡፡  ይህ ዘመን የሚባለው የጊዜ ዕድሜ በስያሜው አጠራር መሠረት ኃላፊ፣ የአሁንና የትንቢት/የወደፊት/  ጊዜ ተብሎ በሦስት ክፍላተ ጊዜ ይመደባል፡፡ «ወፉካሬሁሰ ለዘመን በውስተ ልብ አርአያ ወሰን ውእቱ ለጊዜ ዕድሜ ወዝንቱሰ ጊዜ ዕድሜ ዘስሙ ዘመን ይትከፈል እመንገለ ስሙ ኅበ ሠለስቱ ክፍል ኀበ ዘኅለፈ ዘመነ ወኀበ ዘይመጽእ ወኀበ ዘሀሎሂ እንዲል[1]፡፡

ከጥንተ ፍጥረት እስከ ዳግም ምጽአት ድረስ ያለው ዘመን ሁሉ በእነዚህ ሦስት ጊዜያት ሲሠፈርና ሲቆጠር ይኖራል፡፡ ያለፈውንና የሚመጣውን ዘመን ቆጥሮና ሠፍሮ መረዳትና ማስረዳት  እንደሚገባ ሲገልጽ ደግሞ፣  “ተሰአሉ  ዘቀደሙ መዋዕለ ዘኮነ እምቅድሜክሙ እምአመ ፈጠሮሙ እግዚአብሔር ለእጓለ እመሕያው ዲበ ምድር እም አጽናፈ ሰማይ እስከ አጽናፈ ሰማይ ለእመ ኮነ ዝንቱ ነገር፤ እግዚአብሔር  ሰውን በምድር ላይ ከፈጠረው ጀምሮ ከሰማይ ዳር እስከ ዳርቻዋ ድረስ ከቶ እንዲህ ያለ ታላቅ ነገር ወይም እንደ እርሱ ያለ ተሰምቶ እንደሆነ ከአንተ በፊት የነበረውን የቀድሞው ዘመን ጠይቅ”  ተብሎ ተጽፏል /ዘዳ.4÷32 ፡፡

ልበ አምላክ ዳዊትም ያለፈውን ዘመን በማስታወስ “የድሮውን ዘመን አሰብሁ፤ የዘለዓለሙን ዓመታት አሰብሁ፤ አጠነጠንሁም” በማለት ተናግሯል /መዝ.76÷51/፡፡

ዳግመኛም ይህ ዓመታትን ቆጥሮ ዘመኑን ያወቀው ልበ አምላክ ዳዊት ሲጸልይ፣ “ንግረኒ ውኅዶን ለመዋዕልየ፤ የዘመኔን አነስተኛነት ንገረኝ” ብሏል/መዝ.101÷23፡፡ ክቡር ዳዊት የዘመኑን ቁጥር ሲያሰላ እየቀነሰ እንደሚሔድ ገብቶታል፡፡ ይህ ግን ከኃጢአቱ የተነሣ አይደለም፡፡ ይልቁንም ስለ እርሱ የተጻፈው ምሥክርነት “ዳዊትም በራሱ ዘመን የእግዚአብሔርን አሳብ ከገሰገሰ በኋላ አንቀላፋ”  ይላል/ሐዋ.13÷37/፡፡ ይህ ደግሞ ዘመንን ታረዝማለች፡፡ እንዲል /ምሳ.10÷27/

በመሆኑም ኦርቶዶክሳውያን አባቶቻችንን ሥርዓት ጠብቀን፣ ሕገ እግዚአብሔርን አክብረን፣ እግዚአብሔር ሠፍሮ የሰጠንን ዘመን እርሱ በገለጸልን አቆጣጠር እየተጠቀምን በየዓመቱ አጽዋማትን እንጾማለን፣ በዓላትን እናከብራለን፡፡ በመሆኑም እንደእስካሁኑ ሁሉ ዛሬም የ2011 ዓ.ም አጽዋማትንና በዓላትን እንደሚከተለው እናወጣለን፡፡

                                                                  መባጃ ሐመር
ለአጽዋማትና በዓላት ማውጫ ወሳኝ የሆነው ነጥብ መባጃ ሐመር ነው፡፡ መባጃ ሐመር መባጊያ ሐመር እየተባለም ይጠራል፡፡ መባጊያ ሐመር ሲሆን የበጋ መመላለሻ የሚል ትርጉም ይሰጣል፡፡ በሌላ በኩል መባጃ በራሱ ማቆያ፣ ማክረሚያ ተብሎ ይተረጎማል፡፡

ሐመር መርከብ፣ መጓጓዣ የሚለውን ትርጉም ያስገኛል፡፡ መባጃ ሐመር የመጥቅዕና የዕለታት ተውሳክ ድምር ሆኖ አጽዋማትና በዓላት የሚውሉበትን ቀን ያመለክታል፡፡ በሐመር የተመሰለውም አጽዋማትና በዓላት ወደ ላይና ወደታች የሚመላለሱበት ሥርዓት /መርከብ/ ስለሆነ ነው፡፡

በአጠቃላይ መባጃ ሐመር ማለት የአጽዋማትንና የበዓላትን መዋያ ወይም መግቢያ ቀን ለማወቅ የሚያገለግል ልዩ ቁጥር ማለት ነው፡፡ [2]

ከሰባቱ አጽዋማት መካከል አራቱ በመባጃ ሐመር መሠረት በየዓመቱ እየተቀያየሩ ወይም ቀመር እየተሠራላቸው የሚወጡ ሲሆን፣ ሦስቱ ግን ያለ መባጃ ሐመር በየዓመቱ በተመሳሳይ ወቅት ይባጃሉ፡፡

በመባጃ ሐመር የሚባጁት አራት አጽዋማት ዐቢይ ጾም፣ ጾመ ድኅነት፣ ጾመ ነነዌና ጾመ ሐዋርያት ሲሆኑ፣ ያለ ማባጃ ሐመር በየዓመቱ ቋሚ ጊዜ ይዘው የሚብቱት ሦስቱ አጽዋማት ደግሞ ጾመ ነቢያት፣ ጾመ ገሃድና ጾመ ማርያም /ፍልሰታ/ ናቸው፡፡

ከላይ በተመለከትነው መሠረት መባጃ ሐመር የአጽዋማትና የበዓላት ማስገኛ ልዩ ቁጥር ነው ካልን ቁጥሩ እንዴት እንደሚገኝ ማወቅ ያስፈልገናል፡፡ መባጃ ሐመርን ለማግኘት መጥቅዕንና በዓለ መጥቅዕ የዋለበትን ዕለት ተውሳክ እንደምራለን፡፡ ይቆየን

ተውሳክ
ተውሳክ ማለት ለአንድ ጾም ወይም ለአንድ ዕለት የተሰጠ ልዩ ቁጥር (ኮድ) ማለት ነው፡፡ በዚህ ቁጥር መሠረትም አጽዋማትንና በዓላትን ማውጣት ይቻላል፡፡

ተውሳክ ማለት ጭማሪ፣ ተጨማሪ ማለት ሲሆን ለበዓላትና ለአጽዋማት ማውጫ ያገለግላል፡፡[3] እንዲል፡፡

መጥቅዕ ማለት ነጋሪት ወይም ደወል ማለት ነው፡፡ ነጋሪት ሲመታ፣ ደወል ሲደወል ሕዝብ ይሰበሰባል፤ መልእክትም ይተላለፋል፡፡ በዓላትና አጽዋማትም በመጥቅዕ ይሰበሰባሉ፤ መዋያቸውንም በዚህ ማወቅ ይቻላል፡፡ በዚህም መሠረት መጥቅዕ ከዕለታት ተውሳክ ጋር ተደምሮ መባጃ ሐመርን ያስገኛል፡፡

      መባጃ ሐመር = መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት ተውሳክ

መጥቅዕ= ያለፈው ዓመት መጥቅዕ + ጥንተ መጥቅዕ (ጥንተ መጥቅዕ በየዓመቱ የማይቀያየር ቁጥር ሲሆን ይኸውም 19 ነው፡፡)

መጥቅዕን በዚህ መንገድ ማግኘት ከቻልን፣ በዓለ መጥቅዕ እንዴት እንደሚገኝ አሁን እንመለከታለን፡፡

‹‹መጥቅዕ ሲበዛ ከመስከረም ንዛ፤ መጥቅዕ ሲያንስ ጥቅምትን ዳስ››

ይህ ታላቅ መልእክት ያለው የአባቶቻችን አባባል ሲሆን ለበዓለ መጥቅዕ ማውጫ የሚያገለግል ንግግራዊ ፎርሙላ ወይም ቀመር ነው፡፡ መጥቅዕ ሲበዛ ከመስከረም ንዛ ማለት በዓለ መጥቅዕን በጥቅምት አውል ማለት ሲሆን፣ መጥቅዕ ሲያንስ ጥቅምትን ዳስ ማለቱ መጥቅዕ ባነሰ ጊዜ በዓለ መጥቅዕን በጥቅምት አውለው ማለት ነው፡፡

መጥቅዕ በዛ የሚባለው ከዐሥራ አራት በላይ ሲሆን ነው፤ አነሰ የሚባለው ደግሞ ከዐሥራ አራት በታች ሲሆን ነው፡፡ በዚህም መሠረት መጥቅዕ ከዐሥራ አራት በላይ ከሆነ በዓለ መጥቅዕ በመስከረም ይውላል፤ መጥቅዕ ከዐሥራ አራት በታች ከሆነ ደግሞ በዓለ መጥቅዕ በጥቅምት ይውላል፡፡ ይህ ሁል ጊዜም ቢሆን የሚያገለግል ሕግ ነው፡፡ ለዚህም ነው አበው ‹‹መጥቅዕ ሲበዛ ከመስከረምንዛ፤ መጥቅዕ ሲያንስ ጥቅምትን ዳስ›› ያሉት፡፡

ለምሳሌ የ2011ን መባጃ ሐመር እንፈልግ፡፡

መባጃ ሐመርን ከመፈለጋችን በፊት ግን መጥቅዕን ማወቅ የግድ ነው፡፡ መጥቅዕን ለማወቅ ደግሞ የወንበርን ዓመታዊ ስሌት ማግኘት ያስፈልጋል፡፡ በመሆኑም፤

ወንበር = ቅልክ+ድልክ – 1

19

=5500+2011 -1

19

=395 ቀሪ 6-1

ወንበር =5

የ2011 ወንበር 5 ነው ማለት ነው፡፡

ከዚህ በመነሣት መጥቅዕን ለማግኘት፤

መጥቅዕ= ወንበር (ጥንተ መጥቅዕ)

= 5(19)

30

= 3 ቀሪ 5

መጥቅዕ = 5

መባጃ ሐመር = መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት ተውሳክ

መጥቅዕ = 5

በዓለ መጥቅዕን ለማግኘት፤ መጥቅዕ ከዐሥራ አራት በታች ስለሆነ ጥቅምት ላይ በዓለ መጥቅዕ ይውላል፡፡ ስለዚህ ጥቅምት 5 ሰኞ በዓለ መጥቅዕ ሲሆን፤ ይህ በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት ሰኞ ተውሳኩ 6 ነው ማለት ነው፡፡

ስለዚህ፤

መባጃ ሐመር = መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋበት ዕለት ተውሳክ

መጥቅዕ = 5

በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት = ሰኞ

የሰኞ ተውሳክ = 6

መባጃ ሐመር = 5 + 6 = 11

ስለዚህ የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር 11 ስለሆነ በዚህ መሠረት የ2011ን በዓላትና አጽዋማት ማውጣት ይቻላል፡፡

የመባጃ ሐመር ዋነኛ አገልግሎት ከአጽዋማት ተውሳክ ጋር እየተደመረ በዓላትንና አጽዋማትን ማስገኘት ነው፡፡ ስለዚህ የአጽዋማትንና የበዓላትን ተውሳክ ማወቅ ይጠበቅብናል፡፡በመሆኑም መባጃ  ሐመሩንና የበዓላትና የአጽዋማትን ተውሳክ በመጠቀም የ2011ን የበዓላትና የአጽዋማትን መግቢያ እናገኛለን፡፡

ጾመ ነነዌ
ጾመ ነነዌ የራሱ የሆነ ተውሳክ የለውም፡፡ የሚወጣውም ያለ ተውሳክ በመባጃ ሐመር ብቻ ነው፡፡

ሀ. በዓለ መጥቅዕ በመስከረም በሚውልበት ጊዜ ጾመ ነነዌ በጥር ይውላል፡፡

ለ. በዓለ መጥቅዕ በጥቅምት በሚሆንበት ጊዜ ጾመ ነነዌ በየካቲት ይውላል፡፡

ሐ. መጥቅዕ ከ፲፬(14) በላይ ሆኖ ከዕለት ተውሳክ ጋር ስንደምረው ከ፴(30) ከበለጠ ጾመ ነነዌ በየካቲት ይውላል፡፡

ከላይ የተዘረዘሩት አራት ነጥቦች መቼም ቢሆን የማይለወጡ ቋሚ ሕጎች ናቸው፡፡ በመሆኑም እነዚህን አራቱን በቃል አጥንቶ መያዝ ያስፈልጋል፡፡

ምሳሌ፡- ከላይ የተመለከትነውን የ2011 ዓ.ምን ጾመ ነነዌ እናውጣ፡፡

መጥቅዕ 5 ሲሆን በዓለ መጥቅዕ ጥቅምት ሰኞ ነው፡፡ መባጃ ሐመሩ ደግሞ 11 ነው፡፡ ከላይ በ‹‹ለ››እንደተመለከትነው በዓለ መጥቅዕ በጥቅምት በሚሆንበት ጊዜ ጾመ ነነዌ በየካቲት ይውላል ብለናል፡፡ በተጨማሪም ጾመ ነነዌ ተውሳክ ስለሌላት በመባጃ ሐመርብቻ ነው የምትወጣ ብለናል፡፡ ስለዚህ መባጃ ሐመሩ 11 ስለሆነ የካቲት 11 ቀን ጾመ ነነዌ ትገባለች ማለት ነው፡፡

ዐቢይ ጾም
የዐቢይ ጾምን ተውሳክ ለማግኘት ከጾመ ነነዌ ማግስት ጀምሮ እስከ ዐቢይ ጾም ያሉትን ቀናት መቁጠር ነው፡፡ እኒህም ቀናት ፲፬(14) ናቸው፡፡ በመሆኑም የዐቢይ ጾም ተውሳክ ፲፬(14) ነው ማለት ነው፡፡

ለምሳሌ በ2011 ዓ.ም ዐቢይ ጾም የገባው፤

የዐቢይ ጾም መግቢያ = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የዐቢይ ጾም ተውሳክ

መባጃ ሐመር = 11

የዐቢይ ጾም ተውሳክ = ፲፬(14)

የዐቢይ ጾም መግቢያ = 11 + 14 = 25

የካቲት 25 የዐቢይ ጾም መግቢያ ነው ማለት ነው፡፡

ደብረ ዘይት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ዐቢይ ጾም ያሉትን ቀናት ቆጥረን የዐቢይ ጾም ተውሳክ ፲፬(14) ነው ብለናል፡፡ የደብረ ዘይትን ተውሳክ ለማግኘትም በተመሳሳይ መልኩ ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ደብረ ዘይት ያሉትን ቀናት ስንቆጥር ፵፩(41) ቀናትን እናገኛለን፡፡ ለ፴(30) ሲካፈል ቀሪ (፲፩)11ን እናገኛለን፡፡ ስለዚህ የደብረ ዘይት ተውሳክ ፲፩(11) ነው ማለት ነው፡፡

ደብረ ዘይት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የደብረ ዘይት ተውሳክ

= 11 + 11

= 22

ከየካቲት ቀጥሎ ያለው ወር መጋቢት ስለሆነ መጋቢት 22 ደብረዘይት ነው ማለት ነው፡፡

ሆሣዕና
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ሆሣዕና ያሉት ቀናት ፷፪(62) ናቸው፡፡ እንደተለመደው ለ፴(30) ስናካፍለው ፪(2) ቀሪ እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የሆሣዕና ተውሳክ (፪)2 ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ሆሣዕና መግቢያ = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የሆሣዕና ተውሳክ

= 11 + 2

= 13

ሚያዝያ 13 በዓለ ሆሣዕና ነበር ማለት ነው፡፡

ስቅለት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ስቅለት ያሉት ቀናት ሥልሳ ሰባት ናቸው፡፡ ለሠላሳ ስናካፍለው ቀሪ ፯(7)ን እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የስቅለት ተውሳክ ፯/7/ ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ስቅለት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የስቅለት ተውሳክ

= 11 + 7

= 18

ሚያዝያ 18 ስቅለት ነው ማለት ነው፡፡

ትንሣኤ
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ትንሣኤ ያሉት ቀናት ሥልሳ ዘጠኝ ናቸው፡፡ ለሠላሳ ስናካፍለው ቀሪ ፱(9) እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የትንሣኤ ተውሳክ ፱ (9) ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ትንሣኤ = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የትንሣኤ ተውሳክ

= 11 + 9

= 20

ሚያዝያ 20 ትንሣኤ ነው ማለት ነው፡፡

ርክበ ካህናት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ርክበ ካህናት ያሉት ቀናት ፺፫(93) ናቸው፡፡ ለሠላሳ ስናካፍለውቀሪ ፫(3)ን እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የርክበ ካህናት ተውሳክ ፫(3) ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ርክበ ካህናት = የ2011 መባጃ ሐመር + የርክበ ካህናት ተውሳክ

= 11 + 3

= 14

ግንቦት 14 ርክበ ካህናት ነው ማለት ነው፡፡

ዕርገት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ በዓለ ዕርገት ያሉት ቀናት ፻፰(108) ናቸው፡፡ ፻፰(108)ን ለ፴(30) ስናካ ፍለው ፫(3) ጊዜ ደርሶ ፲፰(18) ይቀራል፡፡ በመሆኑም የዕርገት ተውሳክ ፲፰(18) ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ዕርገት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የስቅለት ተውሳክ

= 11 + 18

= 29

ግንቦት 29 ዕርገት ነው ማለት ነው፡፡

ጰራቅሊጦስ
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ጰራቅሊጦስ ያሉት ቀናት ፻፲፰(118)ናቸው፡፡ ፻፲፰(118)ን ለ፴(30) ስናካፍለው ፫(3) ቀሪ ፳፰(28) ይሆናል፡፡

፳፰(28) የጰራቅሊጦስ ተውሳክ ይሆናል፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ጰራቅሊጦስ = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የጰራቅሊጦስ ተውሳክ

= 11 + 28

= 39

ለ፴(30) ሲካፈል 9 ቀሪ ይሆናል፡፡ ጰራቅሊጦስ ሰኔ 9 ነው ማለት ነው፡፡

ጾመ ሐዋርያት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ጾመ ሐዋርያት ያሉት ቀናት ፻፲፱(119) ናቸው፡፡ ፻፲፱ (119)ን ለ፴(30) ስናካፍለው ፫(3) ጊዜ ደርሶ ፳፱ (29) ይቀራል፡፡

፳፱(29) የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ጾመ ሐዋርያት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ

= 11 + 29

= 40

40 ለ30 ሲካፈል 1 ቀሪ 10 ይሆናል፡፡

ስለዚህ ሰኔ 10 የጾመ ሐዋርያት መግቢያ ነው ማለት ነው፡፡

ጾመ ድኅነት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ጾመ ድኅነት ያሉት ቀናት ፻፳፩(121) ናቸው፡፡ ፻፳፩(121) ለ፴(30) ሲካፈል ፬(4) ጊዜ ደርሶ ፩(1) ይቀራል፡፡ የጾመ ድኅነት ተውሳክ ፩(1) ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ጾመ ድኅነት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የጾመ ድኀነት ተውሳክ

= 11 + 1

= 12

ሰኔ 12 የጾመ ድኅነት መግቢያ ዕለት ነው ማለት ነው፡፡

በአጠቃላይ የአጽዋማቱ ተውሳክ እንደሚከተለው ነው፡፡

አጽዋማት       ተውሳክ           የመዋያ ዕለት

ጾመ ነነዌ        = አልቦ (0)         የካቲት 11

ዐቢይ ጾም        = ፲፬(14)           የካቲት 26

ደብረ ዘይት       = ፲፩(11)          መጋቢት 22

ሆሣዕና          = ፪(2)             ሚያዝያ 13

ስቅለት           = ፯(7)             ሚያዝያ 18

ትንሣኤ          = ፱(9)             ሚያዝያ 20

ርክበ ካህናት      = ፫(3)             ግንቦት 14

ዕርገት           = ፲፰(18)          ግንቦት 29

ጰራቅሊጦስ       = ፳፰(28)          ሰኔ 9

ጾመ ሐዋርያት    = ፳፱(29)          ሰኔ 10

ጾመ ድኅነት       = ፩(1)            ሰኔ 12

ኢየዐርግና ኢይወርድ
እነዚህ አጽዋማት ምንም እንኳን በየዓመቱ የየራሳቸው ቀመራዊ ማውጫ ቢኖራቸውም ገደብ ግን አላቸው፡፡ ገደባቸውም በግእዝ ኢይወርድና ኢየዐርግ ሲባል፣ ኢይወርድ የታችኛው እርከን፣ ኢየዐርግ ደግሞ የላይኛው እርከን ነው፡፡ በአማርኛው ገደብ ልንለው እንችላለን፡፡ በዚህም መሠረት የአጽዋማት ገደብ የሚከተለውን ይመስላል፡፡

አጽዋማትና በዓላት          ኢይወርድ    ኢየዐርግ

ጾመ ነነዌ             ጥር 17             የካቲት 21

ዐቢይ ጾም           የካቲት 1             መጋቢት 5

ደብረ ዘይት          የካቲት 28            ሚያዝያ 2

ሆሣዕና             መጋቢት 19           ሚያዝያ 23

ስቅለት          መጋቢት 24           ሚያዝያ 28

ትንሣኤ            መጋቢት 26           ሚያዝያ 30

ርክበ ካህናት        ሚያዝያ 20             ግንቦት 24

ዕርገት             ግንቦት 5                ሠኔ 9

ጰራቅሊጦስ         ግንቦት 15               ሠኔ 19

ጾመ ሐዋርያት      ግንቦት 16               ሠኔ 20

ጾመ ድኅነት        ግንቦት 18               ሠኔ 22

ቋሚ የመግቢያ ጊዜ ያላቸው አጽዋማት
                               ጾመ ነቢያት
ጾመ ነቢያት በአራቱም ዘመናት ምን ጊዜም ኅዳር ዐሥራ አምስት እንዲጾም ተወስኗል፡፡

                                   ጾመ ገሀ  ድ
ጾመ ገሀድ የትክ ጾም ነው፡፡ ይህ ጾም ዓርብንና ሮብን የሚያሽር በዓል በዓርብና በሮብ ሲውል በትኩ በዋዜማው የሚጾም ጾም ነው፡፡ ለምሳሌ ጥምቀት ዓርብ ቢውል ሐሙስ ጾመ ገሀድ ይሆናል፡፡ ነገር ግን አበው ለጾም ማድላት አለብን በማለት ጾመ ገሀድ ምንጊዜም ጥምቀት በጾም ቀን ዋለም አልዋለም በዋዜማው እንዲጾም ወስነዋል፡፡

                                   ጾመ ፍልሰታ 
ሐዋርያት የእመቤታችንን ትንሣኤ ለማየት ይበቁ ዘንድ ሱባኤ ገብተው የጾሙት ጾም ሲሆን ምንጊዜም ነሐሴ አንድ ቀን ገብቶ ከሁለት ሱባኤ በኋላ የእመቤታችን ዕርገት ይፈጸማል፡፡

[1]  አቡሻኸር አንቀጽ 1 ገጽ 17 (የብራና ጽሑፍ)

[2] ዲ/ን ታደለ ሲሳይ ባሕረ ሐሳብ በቀላል አቀራረብ ገጽ 71

[3]  ዝኒ ከማሁ ገጽ 66

እምቤተ ክህነት ወመንግሥት ዘኀረይዋ ይእቲኬ ማርያም ድንግል

           በዲ/ን ታደለ ሲሳይ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትኩረት አድርጋ የምታከብራቸው በርካታ የቅዱሳን በዓላት አሉ፡፡ የእመቤታችን ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም በዓላትም በቤተ ክርስቲያኗ ሰፊ ቦታ ተሰጥተው የሚከበሩ ናቸው፡፡ ለአብነት ያህልም በየዓመቱ ግንቦት አንድ ቀን የሚከበረውን የቅድስት ድንግል ማርያምን የልደት በዓል መመልከት ይቻላል፡፡ ለሃይማኖታችን መሠረት፣ ለክርስትናችን ዋስትና፣ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ስንቅ የሆኑት ቅዱሳት መጻሕፍት እንደሚያስረዱን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ግንቦት 1 ቀን በ15 ዓ.ዓ  ቅድመ ልደተ ክርስቶስ መወለዷን እንረዳለን፡፡ ይሁን እንጂ አንዳንድ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲን፣ ቅዱሳት መጻሕፍትና ሌሎች አብያተ ክርስቲያናት የእመቤታችን ልደት መስከረም 10 በማለት ያከብራሉ፡፡ ይህንንም የተኣምረ ማርያም መቅድም «ወቦ እለ ይቤሉ አመ ዐሡሩ ለመስከረም ልደታ፤ መስከረም 10 ቀን ልደቷ ነው የሚሉ አሉ» ይላል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ግን በዐዋጅ ግንቦት 1 ቀን ታከብረዋለች፡፡ ወላጆችዋም ኢያቄምና ሐና ይባላሉ፡፡ አባትዋ ኢያቄም ከቤተ ይሁዳ (ከይሁዳ ነገድ) ሲሆን፣ እናትዋ ሐና ከቤተ ሌዊ (ከነገደ ሌዊ) ናት፡፡ የተወለደችበት ሀገርም ናዝሬት ይባላል፡፡

       የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ግን በዐዋጅ ግንቦት 1 ቀን ታከብረዋለች፡፡ ወላጆችዋም ኢያቄምና ሐና ይባላሉ፡፡ አባትዋ ኢያቄም ከቤተ ይሁዳ (ከይሁዳ ነገድ) ሲሆን፣ እናትዋ ሐና ከቤተ ሌዊ (ከነገደ ሌዊ) ናት፡፡ የተወለደችበት ሀገርም ናዝሬት ይባላል፡፡የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የዘር ሐረግ ነገደ ይሁዳና ነገደ ሌዊ መሆኑን በተለያዩ ቅዱሳት መጻሕፍት ተመዝግቦ እናገኘዋለን፡፡ ለአብነት ያህልም ሊቁ ቅዱስ ያሬድ «ትወጽእ በትር እምሥርዎ እሴይ ወየዐርግ ጽጌ ይእቲ በትር አምሳለ ማርያም ቅድስት ይእቲ ወጽጌ ዘይወጽእ እምኔሃ አምሳሉ ለወልድ……..” በትር ከእሤይ ሥር ትወጣለች አበባም ከእርስዋ ይወጣል፤ በትር የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ናት» በማለት እመቤታችን ከዳዊት ዘር መሆንዋን ይገልጻል፡፡ ይህንንንም ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴ ማርያም ድርሰቱ « አንቲ ውእቱ ዘመድ ዘእምሥርወ ዳዊት፤ ከዳዊት ዘር የተገኘሽ ዘመድ አንቺ ነሽ» ሲል ያጠነክረዋል፡፡ «በሩካቤ ዘበሕግ እለ ወለድዋ እምቤተ ክህነት ወመንግሥት ዘኀረይዋ ይእቲኬ ማርም ድንግል፤ በሕጋዊ ሩካቤ የወለዱአት ከቤተ ክህነት እና ከቤተ መንግሥት የመረጡአት ድንግል ማርም ናት» በማለት ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ከቤተ መንግሥትና ከቤተ ክህነት መመረጧን ይገልጻል፡፡ (ድጓ ዘነሐሴ)
ወደ ጥንተ ነገራችን ስንመለስ፣ ኢያቄምና ሐና በመጀመሪያ ልጅ መውለድ ተስኖአቸው ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት ልጆች ባሏቸው ሰዎች ሁሉ መንፈሳዊ ቅንዓት ያድርባቸው ነበር፡፡ በመዝሙረ ዳዊት «ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታዎች ናቸው» (መዝ. 126÷3) ተብሎ ስለተጻፈ ልጅን መመኘት መንፈሳዊ ፍላጎት ነውና ኢያቄምና ሐናም አጥብቀው ይሹ ነበር፡፡ የኢያቄምና የሐና ልጅ ማጣት ግን እጅና እግራቸውን አጣጥፈው እንዲቀመጡ አላደረጋቸውም፡፡ ይልቁንም «አንኳኩ ይከፈትላችኋል» እንደተባለው እግዚአብሔር አምላክ በቸርነቱ በልጅ ይጎበኛቸው ዘንድ አጥብቀው ይጸልዩ ነበር እንጂ፡፡ (አንዳንድ ሰዎች በትዳር ሕይወታቸው ልጅ መውለድ በተሳናቸው ጊዜ እንደ ሐናና ኢያቄም በጸሎት ከመትጋት ይልቅ መከነች መከነ ብዬ ላልክድሽ ላልክድህ ተባብለው የገነቡትን ትዳር ወደማፍረስ መሄዳቸው የሐናንና የኢያቄምን መንፈሳዊ የትዳር ተሞክሮ አለመቅሰም ነው፡፡) ጸሎታቸውም የሚጦረን፣ የሚንከባከበን፣ ርስታችንን የሚወርስልን ልጅ ስጠን ሳይሆን፣ ሰውንና እግዚአብሔርን የሚያስደስት፣ ለቤተ እግዚአብሔር የሚገባ፣ አንተን የሚስደስት ልጅ ስጠን የሚል ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት በልጅ ቢጎበኛቸው ልጃቸውን ለእግዚአብሔር እንደሚሰጡ ተሳሉ፡፡
ከዚህም በኋላ የለመኑትን የማይነሳ፣ የነገሩትን የማይረሳው ልዑል እግዚአብሔር የሐናን ማኅጸን በጽንስ ጎበኘው፡፡ ይህም የሆነው ነሐሴ ሰባት ቀን ነው፡፡ ከዚያም ግንቦት አንድ ቀን፣ እሙ ለፀሐየ ጽድቅ፣ መድኃኒታ ለሔዋን፣ የኖኅ ቃልኪዳን፣ የአዳም ተስፋ፣ ላዘኑ መጽናኛቸው፣ ለተሰደዱ ተስፋቸው፣ ለተራቡ ምግባቸው፣ ለታረዙ ልብሳቸው፣ ንጽሕት በድንግልና ሥጋ ወሕሊና የሆነች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደች፡፡ጽንሰቷም ሆነ ልደቷ ርኩሰት የሌለበት፣ በቅድስና የተመላ፣ በሕግ የጸና ነው፡፡ «ኦ ድንግል አኮ በፍትወተ ደነስ ዘተጸነስኪ አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ፤ ድንግል ሆይ በጢአት ፍትወት (በዝሙት በርኩሰት) የተፀነስሽ አይደለሽም፤ በሕግ፣ በሩካቤ፣ በሥርዓት ከሐናና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጅ» እንዳለ (አባ ሕርያቆስ፤ ቅዳሴ ማርያም

         የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም መወለድ ለጊዜው ደስታው ለኢያቄምና ሐና ቢሆንም በመጨረሻ ግን ለዓለም ነው፡፡ እመቤታችን በመጀመሪያ ለኢያቄምና ሐና ብትሰጥም ፍጻሜው ግን የዓለም ስጦታ ናት፡፡ ምክንያቱም የድኅነታችን ዘውድ ናትና፡፡ (ቅዳሴ ማርያም)
አዳምና ሔዋን ትእዛዘ እግዚአብሔርን ተላልፈው የሞት ሞት በተፈረደባቸው ጊዜ እግዚአብሔር ተስፋ የሰጣቸው ከልጅ ልጃቸው ተወልዶ እንደሚያድናቸው ነው፡፡ ይህም በብሉይ ኪዳን በትንቢት ሲነገር ነበር፡፡ በትንቢተ ኢሳይያስ ላይ በትር ከእሴይ ግንድ ይወጣል ተብሎ የተነገረው ትንቢትም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የዓለምን መድኅን ለመውለድ እንደምትወለድ የሚገልጽ ነበር፡፡ (ኢሳ. 11÷1) ከላይ እንደተገለጸው የአዳም የልጅ ልጅ የተባለችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፡፡ ይህንን ቃል ኪዳን ሲሰጣቸው አዳምና ሔዋን በተስፋ መኖር ጀምረዋል፡፡ በኋላም ግንቦት አንድ ቀን እመቤታችን ስትወለድ የአዳም የድኅነት ቀን መድረሱ ታውቋል፡፡ ለዚህም ነው አባ ሕርቆስ «አንቲ ውእቱ ተስፋሁ ለአዳም አመ ይሰደድ እምገነት፤ ከገነት በተሰደደ ጊዜ የአዳም ተስፋው አንቺ ነሽ» (ቅዳሴ ማርያም) ያለው፡፡ ከገነት ተባሮ በረከቱን ሲገፈፍ የተሰጠው ቃል በእርሷ መወለድ እንደሚድን ነበርና፡፡ እግዚአብሔር አዳምን ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ ሲለው፣ ለድኅነቱ ምክንያት የሆነች የልጅ ልጁን መወለድ ተስፋ ያደርግ ነበርና፣ ምክንያተ ድኂን ቅድስት ድንግል ማርያም መወለዷ ለአዳምና ለልጆቹ ትልቅ ክብርና የብርሃን ተስፋ ነው፡፡
የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም መወለድ ለአዳም መዳን ምክንያት እንደሆነ ሁሉ ለሰው ልጆች፣ እንዲሁም በኃጢአት ለተወሰደው ዓለም ሁሉ ከኃጢአቱ ነጽቶ በሥራው ገነት መንግሥተ ሰማያትን ይወርስ ዘንድ የሚችልበት መንገድ የተጠረገበት ነው፡፡ ምክንያቱም በመጀመሪያ ቀዳማዊ አዳምና ቀዳሚት ሔዋን በሠሩት ጥፋት የመጣው ሞት የተሻረው በዳግሚት ሔዋን (በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም) መወለድና ዳግማዊ አዳምን (መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን) በመውለድ ነውና፡፡ ሔዋን ያመጣችው መርገም በእመቤታችን ቀርቷል፤ አዳም ያመጣው ሞት በክርስቶስ ድል ተደርጓልና፡፡የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ልደት በድቅድቅ ጨለማ የነበረው ዓለም ብርሃንን ያየበት ነው፡፡ ዓለም ለአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ያህል በዲያብሎስ ቁራኝነት፣ በኃጢአት ሞት ጨለማነት፣ ተይዞ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ይህን ጨለማ ለማስወገድም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ኆኅተ ምሥራቅ ሆና፣ በእርሷም ፀሓየ ጽድቅ ኢየሱስ ክርስቶስ ወጥቶ ለዓለም ሁሉ ብርሃን ሆኖአል፡፡ «ብርሃን ዘበአማን ዘያበርህ ለኩሉ ሰብእ ለእለ ይነብሩ ውስተ ዓለም፤ በዓለም ውስጥ ለሚኖሩ ሰዎች ሁሉ የሚያበራ እውነተኛ ብርሃን እርሱ ነው» እንዲል ቅዱስ ኤፍሬም በሰኞ ውዳሴ ማርያም፡፡
እኛም ብርሃንን ወልዳልናለችና እሙ ለብርሃን፣ የዓለም ፀሓይ ከእርሷ ተገኝቷልናልና ኆኅተ ምሥራቅ፣ ለመዳናችን ምክንያት ናትና ምክንያተ ድኂን፣ የአዳም ተስፋው ናትና ተስፋሁ ለአዳም እያልን የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ልደት እናከብራለን፡፡የበጎ ነገር ሁሉ ጠላት የሆነው ዲያብሎስ ክብረ ድንግል ማርያምን ደብቆ ለማስቀረት ደፋ ቀና ቢልም፣ እኛ ግን ብርሃንን አይተንባታልና ልደቷን እንደ አባቶቻችን በማኅሌት፣ በቅዳሴና በሌሎች አገልግሎቶች እያከበርን «ዮም ፍስሓ ኮነ በእንተ ልደታ ለማርያም፤ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ልደት አማካኝነት ዛሬ በዓለም ሁሉ ደስታ ሆኗል» እያልን እንዘምራለን፡፡ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በረከትና ረድኤት ይክፈለን አሜን
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ክብረ ቅዱሳን እና ዐሥሩ መዓርጋት

በሊቀ ማእምራን ደጉ ዓለም ካሣ

ሚያዝያ ፳፪ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

‹ቅዱሳን› ማለት ‹የተቀደሱ፣ የከበሩ፣ የተመሰገኑ፣ የተለዩ፣ የተመረጡ፣ ንጹሐን የኾኑ፣ የጠሩ› ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር ቅዱስ ነውና የጌትነቱ መገለጫ የኾኑ ዂሉ ቅዱሳን ይባላሉ፡፡ ቅዱሳን፣ በሃይማኖት ጸንተው፣ በምግባር ጐልምሰው፣ የሥጋ ምኞታቸውን ትተው ሲገኙ የቅድስና ባለቤት ቅዱስ እግዚአብሔር እነርሱን (ቅዱሳንን) መሣሪያ አድርጐ ኀይሉንና ሥልጣኑን የገለጸባቸው ማኅደረ እግዚአብሔር (የእግዚአብሔር ማደሪያ) ናቸው፡፡ ቅዱሳን እንደ መላእክት ውሉደ እግዚአብሔር (የእግዚአብሔር ልጆች) ይባላሉ (ኢዮ. ፩፥፮፤ ሮሜ. ፰፥፲፬)፡፡

ቅዱሳን፣ በግብር መላእክትን መስለው፣ ኾነው የእግዚአብሔርን ፈቃድ ፈጽመው በመገኘታቸውና ከዚህ ዓለም ፈቃድ በመለየታቸው ቅዱሳን፤ የፈጣሪያቸውን መንግሥት ወራሾች በመኾናቸው ደግሞ ‹ውሉደ እግዚአብሔር› (የእግዚአብሔር ልጆች) ይባላሉ፡፡ በሌላም ቃል ‹ውሉደ ብርሃን› (የብርሃን ልጆች) ተብለው ይጠራሉ (ሉቃ. ፲፮፥፰)፡፡ ‹ውሉደ ሕይወት› (የሕይወት ልጆች) ይባላሉ፤ ሞትንና የሞት ከተማ የኾነውን ይህን ዓለም ንቀውታልና፡፡ በክብር ተነሥተው ዳግመኛ ሊሞቱ የማይገባቸው ናቸውና (ሉቃ. ፳፥፴)፡፡ ቅዱሳን፣ ‹ውሉደ ጥምቅት› (የጥምቀት ልጆች) ተብለዋል፤ ሀብተ ወልድናን (የእግዚአብሔርን ልጅነት)፣ ስመ ክርስትናን ተጐናጽፈዋልና፡፡ ‹ውሉደ መንግሥትም› ተብለዋል፤ የመንግሥተ ሰማያት ባለቤቶች ናቸውና፡፡

ቅዱሳን፣ በጸጋ እግዚአብሔር በመበልጸጋቸው ወይም የእግዚአብሔር የምሕረቱ ዓይኖች በመኾናቸው ‹አዕይንተ እግዚአብሔር› (የእግዚአብሔር ዓይኖች) ተብለዋል (መዝ. ፴፫፥፲፭)፡፡ ልመናቸው፣ ጾማቸው፣ ምጽዋታቸው ዂሉ የተወደደ መሥዋዕት ነው፡፡ ቅዱሳን በዓላማቸው ጾምን ግብዣ (ድግስ)፣ ለቅሶን ደስታ፣ ደስታን ሐዘን አድርገው በመኖራቸው ይህ ተለዋዋጭ ዓለም በየጊዜው የሚያቀርብላቸው መርዶ በእነርሱ ዘንድ ዋጋ የለውም፡፡ ዓለምም ለእነርሱ የሚያቀርበው ዓለማዊ የምኞት ስጦታ እንደ ኢ ምንት የተናቀ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ገጸ መዓቱ ወደ ዓለማውያን ሰነፎች እንደ ኾነ ዂሉ ገጸ ምሕረቱ ደግሞ ወደ ቅዱሳን ነው፡፡ የእግዚአብሔር ፈቃድና ቸርነት መገለጫዎችም ናቸውና፡፡ ስለዚህ አማላጅነታቸው፣ ጸሎታቸው ጠቃሚ ነው፡፡

‹‹አፍቅርዎ ለእግዚአብሔር ኵልክሙ ጻድቃኑ እስመ ጽድቀ የኀሥሥ እግዚአብሔር፤ ቅዱሳን፣ እውነትን ይዛችሁ ትሕትናን ተላብሳችሁ እግዚአብሔርን ውደዱት፡፡ እግዚአብሐር እውነትን፣ ትሕትናን ይወዳልና፤›› (መዝ. ፴፥፳፫) ተብሎ እንደ ተጻፈ፣ የቅዱሳን ፍሬ ትሕትና ነው፡፡ በዓይነ ሕሊናቸው ፈጣሪያቸውን፣ በዓይነ ሥጋቸው የእነርሱን ምንነት እንደዚሁም የዓለምን ከንቱነት ይመለከታሉ፡፡ ፍሬ የያዘ ተክል ዂሉ ቁልቁል የተደፋ መኾኑ ትሕትናን ያስተምራል፡፡ ይህም የጻድቃን ምሳሌ ነው፡፡ በፈሪሃ እግዚአብሔር ልቡ የተሰበረ፣ እሱርነቱን (ማንነቱን፣ ምንነቱን) የመረመረ ሰው በዓይነ ሕሊናው የፈጣሪውን ቸርነት፣ በዓይነ ሥጋው የራሱን ውድቀት ይመለከታል፡፡

ይህ አመለካከት ለጸጋ እግዚአብሔርና ለፍሬ ክብር ያደርሰዋል፡፡ በመቅረዝ ላይ ያለች መብራት መሰወር እንዳይቻላት፣ የመቅረዙ ከፍታ እንደሚገልጻት በተራራ ላይ ያለች ቤትም ለእይታ እንደማትሰወር፣ የተራራው ከፍታ እንደሚገልጻት በጥበበ እግዚአብሔር ከብረው በጸጋ እግዚአብሔር ተውበው የሚኖሩ ቅዱሳን ጻድቃንም ደረጃ በደረጃ መዓርጋትን አልፈው ከመለኮት ባሕርይ ተካፍለው የተአምራት መገለጫ ይኾናሉ፡፡ ‹‹መንክር እግዚአብሔር በላዕለ ቅዱሳኒሁ፤ እግዚአብሔር በቅዱሳኑ በወዳጆቹ አድሮ የሚሠራው ሥራ ድንቅ ነው፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (መዝ. ፷፯፥፴፭፤ ፪ኛ ጴጥ. ፩፥፫)፡፡

ቅዱሳን፣ ከእግዚአብሔር በተሰጣቸው ጸጋ ሙታንን ማስነሣት፣ ዕውራንን ማብራት፣ በአጠቃላይ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን ማድረግ የዘወትር (የዂልጊዜ) ተግባራቸው ነው፡፡ የጸጋና የክብር ባለቤቶች ኾነዋልና በዓለም ላይ ሳሉ የሚመጣባቸውን ፈተና ዂሉ ተቋቁመው የጸጋ መቅረዞች ይኾናሉ፡፡ በዚህ ጸጋቸውም የአናብስቱን አፍ ዘጉ (ዳን. ፯፥፩-፰)፡፡ ውኃውን ወደ ኋላው መለሱ (ዘፀ. ፲፬፥፳፪)፡፡ ዝናም እንዳይሰጥ ሰማይን ለጎሙ (፩ኛ ነገ. ፲፯፥፩፤ ያዕ. ፭፥፲፯)፡፡ ነበልባለ እሳትን አበረዱ (ዳን. ፫፥፩-፲፫)፡፡ የቅዱሳን ወዳጅ እግዚአብሔር አምላካችን ሥጋዊ ሀገረ ተድላን ጥለው፣ ኃላፊ ጠፊ ምድራዊ ምቾታቸውን ንቀው ጸጋውን ከሚጠባበቁት ጋር ዂሉ አብሮ ይኖራል፡፡ ትዕግሥትን የጠዋት ቍርስ፣ የቀን ምሳ፣ የማታ እራት አድርገው የሚመገቧትን ዂሉ ማደሪያ ቤተ መቅደሱ ያደርጋቸዋል፡፡

ቅዱሳን በዚህ ዓለም ይጠበቡበታል፤ ወጥተው ወርደው ሰውነታቸውን ከስስት፣ ኃጢአት ጠብቀው ለወዲያኛው ዓለም ደግሞ በትዕግሥት ደጅ ይጠኑበታል፡፡ ‹‹ፈሪሃ እግዚአብሔር ትፍሥሕተ ልብ ውእቱ ወይሁብ ሐሤተ ወያስተፌሥሕ ወያነውኅ መዋዕለ ሕይወት ለፈራሄ እግዚአብሔር ይሤኒ ደኃሪቱ ወይትባረክ ዕለተ ሞቱ፤ እግዚአብሔርን መፍራት የልብ ደስታ ነው፡፡ ፍጹም የሥጋና የነፍስን ደስታ ይሰጣል፤ በሕይወትም ያኖራል፡፡ እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው ፍጻሜው ያምርለታል፡፡ እንደ ኢዮብ ከደዌው ተፈውሶ ልጅ የልጅ ልጅ አይቶ ይሞታል፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈው ይህ ዂሉ በረከት የቅዱሳን ፍሬ ነው (ኢዮብ ፴፩፥፲፮)፡፡

ቅዱሳን በሚሠሩት ሥራ በያዙት ቅን መንገድ፣ ኢዮባዊ ትዕግሥት፣ አብርሃማዊ ኂሩት፣ ይስሐቃዊ ፈቃደኝነት፣ ያዕቆባዊ ቅን አገልግሎት፣ ዮሴፋዊ ኀዳጌ በቀልነት ሙሴአዊ ለወገን ተቆርቋሪነት እየጨመሩ በመኖራቸው የፈጣሪአቸው ኃይልና ጌትነት እንደዚሁም የድንቅ ሥራው መገለጫዎች ይኾናሉ፡፡ በጸጋ ላይ ጸጋ እየተጨመረላቸው ወደ ዐሥሩ መዓርጋት ይወጣሉ፡፡ ማዕረጋቸውንም ከዚህ ላይ ይናገሩታል፡፡ ዐሥሩ መዓርጋት የሚባሉት በሦስት ይከፈላሉ፡፡ ሦስቱ የንጽሐ ሥጋ መዓርጋት፣ አራቱ የንጽሐ ነፍስ መዓርጋት፣ እና ሦስቱ የንጽሐ ልቡና መዓርጋት ናቸው፡፡

  • ሦስቱ የንጽሐ ሥጋ መዓርጋት የሚባሉት፡- ጽማዌ፣ ልባዌ እና ጣዕመ ዝማሬ ናቸው፡፡
  • አራቱ የንጽሐ ነፍስ መዓርጋት፡- አንብዕ፣ ኵነኔ፣ ፍቅር እና ሑሰት ናቸው፡፡
  • ሦስቱ የንጽሐ ልቡና መዓርጋት ደግሞ፡- ንጻሬ መላእክት፣ ተሰጥሞ እና ከዊነ እሳት (ነጽሮተ ሥሉስ ቅዱስ) ናቸው፡፡ በጠቅላላው ዐሥር ይኾናሉ፡፡

ሀ. የንጽሐ ሥጋ መዓርጋት

፩ኛ መዓርገ ጽማዌ

ይህ የመጀመሪያው መዓርግ ነው፡፡ በዚህ መዓርግ ማስተዋል፣ ውስጣዊ ትዕግሥት፣ ውስጣዊ ትሕትና፣ ውስጣዊ የራስ ሚዛንን ይዞ ማሰላሰል ይጀምራል፡፡ ቅዱሳን ከዚህ መዓርግ ሲደርሱ እግዚአብሔርን ብቻ መዘከር ይችሉ ዘንድ የዚህን ዓለም ውጣ ውረድ ከማውራት ይከለከላሉ፡፡ በዚህ መዓርግ ላይ ሳሉ መላእክት ሲወጡና ሲወርዱ ያየሉ፡፡ ነገር ግን ለምን እንደሚወጡና እንደሚወርዱ አያውቁም፡፡ ዮሐንስ ሐፂር የሰፋውን ስፌት ገበያ ላይ ለመሸጥ ተቀምጦ እያለ በተመስጦ ቅዱስ ሚካኤልንና ቅዱስ ገብርኤልን እንደዚሁም ሌሎች መላእክትን በየመዓርጋቸው እያየ ያደንቅ ነበር፡፡ ስፌቱን የሚገዛ ሰው ቁሞ ‹‹እንቅቡ ዋጋው ስንት ነው?›› ብሎ ሲጠይቀው እርሱ የሚያየውን የሚያይ መስሎት ‹‹ሚካኤልኑ የዓቢ ወሚመ ገብርኤል ሚካኤል፤ ይበልጣል ወይስ ገብርኤል?›› ብሎ በአንክሮ ጠየቀው፡፡ ሰውየውም ‹‹ይኼስ እብድ ነው›› ብሎ ትቶት ሔዷል፡፡

፪ኛ መዓርገ ልባዌ

መዓርገ ልባዌ፣ ማስተዋል፤ ልብ ማድረግ፤ አሰሙኝ እንጂ ስሙኝ አለማለት፤ ልማር እንጂ ላስተምር አለማለት፤ የተነገረው ትንቢትና ተግሣፅ ምዕዳን ዂሉ የራሱ እንደ ኾኑ መገመት፤ መመርመር፤ ዓይነ ሥጋን ከመጽሐፍ፣ ከሥነ ፍጥረት፣ ዓይነ ነፍስን ከምሥጢር ማዋል ነው፡፡ እንደዚሁም የእግዚአብሔርን ቸርነት ማድነቅ፣ ለሰው ልጅ ያደረገዉን ውለታ ማሰላሰል፣ ከሰማየ ሰማያት መውረዱን፣ ከሰው መወለዱን፣ በገዳም መጾሙን፣ መገረፉን፣ ሥጋውን መቍረሱን፣ ደሙን ማፍሰሱን፣ መሰቀሉን፣ መሞቱን፣ መቀበሩን፣ መነሣቱን፣ እያሰቡ ልብን በፍቅረ እግዚአብሔር፤ አንደበትን በመንፈሳዊ ሕይወት መስበር፤ ዓላማን በገጸ መስቀል (ትዕግሥት) መትከል የመሳሰሉት ናቸው፡፡

፫ኛ መዓርገ ጣዕመ ዝማሬ

ከዚህ ደረጃ ሲደረስ አንደበትን ከንባብ፣ ልቡናን ከምሥጢር ማቆራኘት ነው፡፡ ቅዱሳን ከዚህ መዓርግ ሲደርሱ አንደበታቸው ዝም ቢልም በልባቸው ግን ዝም አይሉም፡፡ ከአፍ እስትንፋስ፣ ከአፋፍ ላይ ነፋስ እንደማይለይ ዂሉ ቅዱሳንም ከአንደበታቸው ትዕግሥት፣ ከእጃቸው ምጽዋት፣ ከልቡናቸው ትሕትና፣ ከሰውነታቸው ንጽሕና አይለይም፡፡ የሚጸልዩትና የሚያነቡት ቃል ዂሉ ምሥጢሩ እየገባቸው ስለሚያደርጉት አይሰለቻቸውም፡፡ ከዚህ መዓርግ የደረሰ አንድ ባሕታዊ ለብዙ ዘመናት ‹‹አቡነ ዘበሰማያት›› እያለ ብቻ ሲጸልይ የእግዚአብሔር መልአክ መጥቶ ‹‹‹ይትቀደስ ስምከ› በል እንጂ›› ቢለው ‹‹ኧረ ጌታዬ፥ እኔስ ‹አቡነ ዘበሰማያት› የሚለው ኃይለ ቃል ምሥጢሩና ጣዕሙ በአፌ እንደ ጨው እየሟሟ አልጠገበኝ ብሏል፤ እንዴት አድርጌ ወደ ፊት ልሒድ?›› ብሎታል፡፡

ለ. የንጽሐ ነፍስ መዓርጋት

፩ኛ መዓርገ አንብዕ

ቅዱሳን ከዚህ ማዕረግ ሲደርሱ ኢየሱስ ክርስቶስ (እግዚአብሔር) ለሰው ልጅ ያደረገውን ፍቅር፣ እስከ ሞትና መቃብር የተጓዘውን የመከራ ጉዞ እያሰቡ በአንጻሩም ምረረ ገሃነመ እሳትን ጣዕመ መንግሥተ ሰማያትን እያሰላሰሉ ውሉደ አዳም ይህን ዂሉ መከራ ባለመገንዘብ ወደ ሰፊው የፈቃደ ሥጋ መንገድ ሲጓዝ በማየታቸው ያለቅሳሉ፡፡ ያለምንም መሳቀቅ ሲያለቅሱ እንባቸው እንደ ምንጭ ይፈሳል፤ እንደ ሰን ውኃ ይወርዳል፡፡ ሰዎች ለዚህ ዓለም ድሎት ብለው የሚያለቅሱት ልቅሶ ፊትን ያንጣጣል፤ ዓይንን ያመልጣል፡፡ የቅዱሳን ልቅሶ ግን ፊትን ያበራል፤ ኀጢአትን ያስወግዳል፡፡ እርጥብ እንጨት ከእሳት ጋር በተያያዘ ጊዜ እንጨቱ ከነበልባለ እሳት ሲዋሐድ እንጨቱ እርጥብነቱን ትቶ ውኃውን በአረፋ መልክ እያስወገድ ይነዳል፡፡ ቅዱሳንም በግብር (በሥራ) ከመለኮት ጋር ሲዋሐዱ የዚህ ዓለም ምስቅልቅል ሥራ በሰማያዊ የረጋ ሕይወት ተለውጦ አሠራራቸው፣ አካሔዳቸው ፍጹም፤ ሕይወታቸው መልአካዊ ይኾናል፡፡

፪ኛ መዓርገ ኵነኔ

ቅዱሳን ከዚህ መዓርግ ላይ ሲደርሱ ሥጋዊ ፈቃድ ዂሉ ለነፍስ ፈቃድ ይገዛል፡፡ ነፍስ በሥጋ ባሕርያት ላይ ትሠለጥናለች፡፡ ምድራዊ (ሥጋዊ) ምኞት ዂሉ ይጠፋና መንፈሳዊ (ነፍሳዊ) ተግባር ቦታውን ይወርሳል፡፡ ያለምንም ማወላወል መንፈሳዊ ተግባር ዂሉ ይከናወናል፡፡

፫ኛ መዓርገ ፍቅር

ቅዱሳን ከዚህ ማዕረግ ሲደርሱ እንደ ፈጣሪያቸው እግዚአብሔር ዂሉን አስተካክለው ይወዳሉ፡፡ አማኒ፣ መናፍቅ፣ ኃጥእ፣ ጻድቅ፣ ዘመድ፣ ባዕድ፣ ታላቅ፣ ታናሽ፣ መሐይም፣ መምህር፣ ሳይሉ ዂሉንም አስተካክለው በመውደድ የመፍቀሬ ሰብእ እግዚአብሔር ልጆች መኾናቸውን ይገልጻሉ፡፡

፬ኛ ማዕረገ ሑሰት

ቅዱሳን ከዚህ መዓርግ ላይ ሲደርሱ ባሉበት ኾነው ዂሉን ማየትና መረዳት ይችላሉ፡፡ ጠፈር ሳይከለክላቸው ርቀት ሳያግዳቸው ዂሉን በዂሉ ይመለከታሉ፡፡ 

ሐ. የንጽሐ ልቡና ማዕረጋት

፩ኛ ማዕረገ ንጻሬ መላእክት

ከዚህ ማዕረግ ሲደርሱ መላእክትን ለአገልግሎት ሲወጡ ሲወርዱ ማየት፤ ተልእኳቸውን ያለ ምንም አስተርጓሚ መረዳት፤ ማነጋገርና ማማከር የመሳሰሉትን ዂሉ መፈጸም ይችላሉ፡፡ ለምሳሌ መልአኩን ዐሥር ዓመት እንዳቆመው እንደ ዮሐንስ አፈወርቅ ማለት ነው፡፡

፪ኛ መዓርገ ተሰጥሞ

ቅዱሳን ከዚህ መዓርግ ሲደርሱ በባሕረ ብርሃን መዋኘት፣ ባሉበት ኾነው ወደ ላይም ወደ ታችም መመልከት ይቻላቸዋል፡፡

፫ኛ መዓርገ ከዊነ እሳት (ነጽሮተ ሥሉስ ቅዱስ)

መዓርገ ከዊነ እሳት በሌላ አጠራር ነጽሮተ ሥሉስ ቅዱስ ይባላል፡፡ ይኸውም ሥላሴን በዓይነ ሥጋ ለማየት የሚቻልበት መዓርግ ነው፡፡ ቅዱሳን ከዚህ መዓርግ ሲደርሱ በተዋሕዶ ከመላእክት ጋር ኾነው፣ ረቀው እግዚአብሔርን ማመስገን ይቻላቸዋል፡፡ የለበሱትን ሥጋ ለብቻቸው ለይተው ማየት፤ በአካለ ነፍስ ሰማየ ሰማያትን መጐብኝት፤ ገነት ውስጥ መግባት ይችላሉ፡፡

በአጠቃላይ ‹‹ኩኑ ቅዱሳነ እስመ ቅዱስ አነ›› (ዘሌ. ፲፱፥፪) ተብሎ እንደ ተጻፈው፣ ቅዱሳን የቅዱስ እግዚአብሔር ቤተ መቅደሶች ናቸውና ሕይወታቸው የቅድስና ነው፡፡ ዐሥሩ የቅዱሳን መዓርጋት የሚባሉትም ከላይ የዘረዘርናቸው ናቸው (ዮሐ. ፩፥፵፤ ፪ኛ ጴጥ. ፩፥፬-፲)፡፡ እነዚህም የዐሠርቱ ትእዛዛት ምሳሌዎች ናቸው (ዘፀ. ፳፥፫-፲፯፤ ዘሌ. ፲፱፥፲፰)፡፡ አንድም የዐሥሩ ብፁዓን ምሳሌዎች ናቸው (ማቴ. ፭፥፫-፲፪፤ ዮሐ. ፲፫፥፫፯)፡፡ የቅዱሳን በረከት አይለየን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የጋብቻ ሕይወት እና የሩካቤ ሥርዓት – የመጨረሻ ክፍል

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ   ቀን ፳፻፲ .

ማጠቃለያ

የጋብቻ ሕይወት፣ የሰው ልጅ ፈቃደ ሥጋዉን እንዲፈጽምበት፣ ዘሩን እንዲተካበትና እንዲረዳዳበት እግዚአብሔር አምላካችን ያዘጋጀው ሥርዓት ነው፡፡ በስእለት ወይም በሌላ ምክንያት ለመመንኰስ ከወሰኑ አባቶችና እናቶች በቀር ለሰብአዊ ፍጡር ዂሉ ጋብቻ አስፈላጊ ነው፡፡ ስለዚህ ወይ በጋብቻ አለዚያም በድንግልና መጽናት እንጂ እንዲሁ እየዘሞቱ መኖር ኀጢአት ነው፡፡ ትዳር ለመመሥረት ወስነን ዝግጅት ላይ የምንገኝ ምእመናንም የጋብቻ መሥፈርታችን ሃይማኖትን፣ ክርስቲያናዊ ምግባርንና መልካም ሰብእናን መሠረት ያደረገ ሊኾን ይገባዋል፡፡ ሀብትን፣ ዝናንና ውበትን ምክንያት አድርጎ መተጫጨት መጨረሻው አያምርምና፡፡ እነዚህ ቁሳውያን መሥፈርቶች ከጊዜ በኋላ ሲጠፉ ጋብቻም አብሮ ሊፈርስ ይችላል፡፡ ስለዚህም መሥፈርታችን ከሃይማኖትና ከምግባር ጋር የተገናኘ መኾን ይኖርበታል፡፡ እነዚህ ከተሟሉ ሀብቱና ሌላው ጉዳይ በጊዜ ሒደትና በጥረት የሚመጣ ነውና፡፡

ጋብቻ፣ የመለኮትና የትስብእት ምሳሌ ነው፡፡ ‹‹እፎ ቤተ ነዳይ ኀደረ ከመ ምስኪን፤ እንደ ምስኪን እንዴት ከደሃ ቤት አደረ?›› እንደ ተባለው እግዚአብሔር አምላካችን ለተዋሕዶ የመረጠው የድሆችን ሥጋ ነው፡፡ የተዋሕዶ ምሳሌ የኾነዉን ጋብቻ የምንመሠርት ምእመናንም ሰዎችን ገንዘብ፣ መልክ፣ ዝና የላቸውም ብለን ልንንቃቸውና ከምርጫ ውጪ ልናደርጋቸው አይገባም፡፡ ጋብቻ፣ አንደኛው የሌላኛውን ድክመት እየሸፈነ የሚኖርበት እንጂ በሁለት ፍጹማን ሰዎች የሚመሠረት ሕይወት አይደለም፡፡ ፍጹም አመለካከት ያለዉን ሰው ማግኘት ይከብዳልና፡፡ በመኾኑም ጥንካሬያችንን በመጋራት፣ ድክመታችንን በማስተካከልና በመተራረም ለመኖር መዘጋጀት ይኖርብናል፡፡

በሥራ፣ በአመለካከት ወይም በሞትና በልዩ ልዩ ምክንያት መለያየት ሲመጣ ሕይወታችንን እንዴት እንደምንቀጥልና ሌሎች የመሳሰሉ ጉዳዮችንም መጻሕፍትን በማንበብ፣ ሥልጠና በመውሰድ፣ የልምድ ተሞክሮ ያላቸውን ሰዎች በመጠየቅ ከመተጫጨት በፊት ስለ ጋብቻ ሕይወት ትምህርት ብንቀስም መልካም ነው፡፡ ይህም ለወደፊቱ ሕይወታችን ደስታና ስኬት ይጠቅመናል፡፡ ከዂሉም በላይ እግዚአብሔር አምላካችን መልካምና ታማኝ የትዳር አጋር ይሰጠን ዘንድ በጸሎት መትጋት ይጠበቅብናል፡፡ ከዚሁ ዂሉ ጋርም ጋብቻ የሚከለከልባቸው መንገዶች እንዳሉም መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ እነዚህም ሩካቤን የሚከለክል ደዌ ወይም ተፈጥሯዊ ችግር፣ ምንኵስና (ለመመንኰስ ቃል መግባት)፣ በእምነት መለያየት፣ እንደዚሁም ሥጋዊ፣ መንፈሳዊና የጋብቻ ዝምድናዎች ናቸው፡፡

በሥጋዊ ዝምድና እስከ ሰባት ትውልድ ድረስ መጋባት የተከለከለ ነው፡፡ ስለዚህም በጋብቻ ዝምድና ወደ ላይ፡- ወንድ የአባቱን፣ የአያቱን የቅድመ አያቱን ሚስት፣ ልጅ፣ እኅት፣ እናት አያገባም፡፡ ወደ ታች፡- የልጁን፣ የልጅ ልጁን ልጅ ሚስት፣ ልጅ፣ እኅት፣ እናትና አያት ማግባት ክልክል ነው (ዘሌ. ፲፰፥፮-፳፩፤ ፪፥፩-፳፩)፡፡ ወደ ጎን፡- ወንዱ የወንድሞቹንና የልጆቻቸውን ሚስት ልጅ፣ እኅት፣ እናትና አያት ማግባት አይችልም፡፡ እንደዚሁም የሚስቱን አያት፣ እናት፣ አክስት፣ እኅት፣ ልጅ፣ የልጅ ልጅና በዚህ የዝምድና ሐረግ የሚገኙትን ማግባት አይፈቀድለትም፡፡ መንፈሳዊ ዝምድናን ስንመለከት ደግሞ ወደ ላይ፡- ወንዱ የክርስትና አባቱን ልጅ፣ ሚስት፣ የልጅ ልጅና እኅት፤ ወደ ታች፡- የክርስትና አባት የክርስትና ልጁን እናት፣ እኅት፣ የእኅቱንና የወንድሙን ልጅ ማግባት አይፈቀድለትም (ፍት. ነገ. ፳፬፣ ቍ. ፰፻፵፪-፰፻፶፮)፡፡

እንደዚሁም በእምነት ከማይመስለን ሰው ጋር መጋባት ክልክል ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረው ጋብቻ የኢየሱስ ክርስቶስና የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ነው፡፡ ጋብቻ፣ በሚያምኑና በማያምኑ ሰዎች መካከል ከተፈጸመ ምሥጢሩ ከክርስቶስና ከቤተ ክርስቲያን ተዋሕዶ ጋር አይስማማም፡፡ ስለዚህም በሃይማኖት ከማይመስሉን ጋር መጋባት እንደሌለብን እናስተውል፡፡ በእርግጥ ከአሕዛብ ወይም ከመናፍቃን ወገን የትዳር አጋር የመረጥን ካለን ትምህርተ ሃይማኖትን እንዲማሩና የክርስትና ጥምቀትን እንዲጠመቁ በማድረግ ማግባት እንችላለን (፩ኛ ቆሮ.፯፥፲፪-፲፯፤ ፍት. አን. ፳፬፣ ቍ. ፱፻፲፪-፱፻፲፭)፡፡

ጠቢቡ ሰሎሞን እንደ ቀለበት በልብህ አኑረኝ  በማለት እንደ ተናገረው (መኃ. ፰፥፮)፣ ጋብቻ ለሚጠብቁትና ለሚያከብሩት ሰማያዊ ዋጋ የሚያስገኝ የፍቅርና የአንድነት ሕይወት ነው፡፡ ለቃል ኪዳን የሚታሰረው ክብ ቀለበትም የጋብቻ ሕይወት የማይቋረጥ አንድነት መኾኑን የሚያመላክት ምሥጢር አለው፡፡ በመተጫጨትና በቃል ኪዳን ቀለበት የተመሠረተው ጋብቻ በሥርዓተ ተክሊል ይፈጸማል፡፡ ጋብቻ ምሥጢራዊነቱና ትክክለኛነቱ የሚታወቀው በሥርዓተ ተክሊል ወይም በሥርዓተ ቍርባን ሲፈጸም ብቻ ነው፡፡ ከሥርዓተ ተክሊል ወይም ከቍርባን ውጪ ጋብቻን መፈጸም በሕገ ቤተ ክርስቲያን የተከለከለ ነው (ፍት. ነገ. ፳፬፣ ምዕ. ፳፭፣ ክፍል ፪)፡፡ በድንግልና ጸንተው የቆዩ ምእመናን ጋብቻ በሥርዓተ ተክሊል፤ የመዓስባን (ሁለተኛ የሚያገቡ) ጥንዶች ደግሞ በሥርዓተ ቍርባን ይፈጸማል፡፡ ከሚጋቡት አንዳቸው በድንግልና የቆየ (የቆየች) ከኾነ ለብቻው (ለብቻዋ) ትባረክ ዘንድ ሥርዓት ተሠርቷል (ፍት. ነገ. አን. ፳፬፣ ቍ. ፱፻፮)፡፡

ክርስቲያናዊ ጋብቻ፣ በቃል ኪዳንና በቡራኬ፣ በጸሎተ ተክሊልና በቅዱስ ቍርባን መፈጸሙ ምሥጢርነት አለው፡፡ አንድነቱ ወይም ተዋሕዶው የክርስቶስና የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ነውና (ኤፌ. ፭፥፴፪)፡፡ በሥርዓተ ተክሊል ሙሽሮቹ የሚያደርጉት ቀለበት፣ የሚለብሱት ነጭ ልብስ፣ የሚቀቡት ቅብዓ ቅዱስ፣ የሚቀዳጁት አክሊል፣ እንደዚሁም የካህናቱ ጸሎትና ቡራኬ ሙሽሪትና ሙሽራው ከመንፈስ ቅዱስ ለሚቀበሉት በዓይን ለማይታይ ጸጋ ምክንያቶች ናቸው፡፡ ጸሎቱ ከደረሰ በኋላ ሥርዓተ ቅዳሴ ተደርጎ ሙሽሮቹ ሥጋውንና ደሙን ይቀበላሉ፡፡ ሥጋውና ደሙ የምሥጢራት ዂሉ ማኅተም ነውና፡፡ ያለ ሥጋውና ደሙ ሥርዓተ ተክሊልም ሥርዓተ ቍርባንም አይፈጸምም (ፍት. ነገ. ፳፬፣ መጅ ፩)፡፡ ከሥርዓተ ተክሊልና ከሥርዓተ ቍርባን ሥርዓት ውጪ ጋብቻን መመሥረት በፍጹም ሊለመድ አይገባም፡፡

ክርስቲያን ነን እያልን በሕገ ቤተ ክርስቲያን ካልተመራን ሰው ኾነን ተፈጥረን ሳለን እንደ እንስሳ መኖር ይኾንብናልና በትዳር ያልተወሰንን ወገኖችም የቤተ ክርስቲያናችንን መመሪያ ተቀብለን በሥርዓተ ተክሊል፣ ካልኾነም በሥርዓተ ቍርባን ለመጋባት እንዘጋጅ መልእክታችን ነው፡፡ ከዚህ በፊት በዓለማዊ መንገድ ትዳር የመሠረትን ምእመናንም ንስሐ ገብተን ሥጋዉን ደሙን እየተቀበልን ኑሯችንን ብንቀጥል፣ ለልጆቻችንም ለሌሎች ወገኖችም አብነት መኾን እንችላለን፡፡

ከዚህ በተለየ በሚስት ላይ ሚስት፤ በባል ላይ ባል መደረብ አስጸያፊና በእግዚአብሔር ዘንድ የሚያስጠይቅ ድርጊት መኾኑን ማስተዋል ተገቢ ነው፡፡ ከጋብቻ በፊትም እንኳንስ ከማያገቡት ሰው ጋር ከእጮኛ ጋርም ቢኾን ሩካቤ ሥጋ መፈጸም ኀጢአትም ነውርም ነው፡፡ ከዝሙት እንድትርቁ እግዚአብሔርን እንደማያውቁ አሕዛብ በፍትወት ድል አትነሡ፤ ከእናንተ እያንዳንዱ የራሱን ዕቃ በቅድስና እና በክብር ያገኝ ዘንድ እንዲያውቅ፤” በማለት ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረው ሰውነታችንን በቅድስና መያዝ ይገባናልና (፩ኛ ተሰ. ፬፥፭)፡፡ ይህን በመረዳት በዚህ ዓይነት ኀጢአት የምኖር ምእመናን ከዚህ ክፉ ተግባር መውጣትና ንስሓ መግባት ይኖርብናል፡፡ በንጽሕና የምንኖርም ንጽሕናችንን በመጠበቅ ከሚኾነን ሰው ጋር ጋብቻ መመሥረት፤ ትዳር የመሠረትንም አንድነታችንን ማጥበቅ ይገባናል፡፡ እንደዚህ ብናደርግ በምድርም በሰማይም እንጠቀማለን፡፡

ፍቺን በተመለከተ የጋብቻ ሕይወት ሃይማኖትን፣ ንጽሕናን እንደዚሁም መንፈሳዊ ሕይወትን የሚፈታተን እንደ ዝሙትና ሃይማኖትን መለወጥ ዓይነት ኀጢአት ወይም ሞት ካልመጣ በቀር በአንድነት እንደ ጸና ይኖራል እንጂ በቀላሉ አይፈርስም፡፡ ስለዚህም በጋብቻ አንድነት ውስጥ መለያየት (ፍቺ) እንዳይኖር በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ተደንግጓል፡፡ በመኾኑም ችግሮችን በውይይት በመፍታት፣ በመመካከርና በመፈቃቀር ተስማምቶ እስከ ሞት ድረስ መኖር ተገቢ ነው፡፡ አብሮ ለመኖርና ለሃይማኖት እንቅፋት የሚኾኑ፣ የጋብቻን ክብር የሚያቃልሉ ለምሳሌ ሩካቤ ሥጋ ለመፈጸም አለመቻል፣ ሃይማኖትን መለወጥ፣ በትዳር ላይ መሴሰንና የመሳሰሉ እንቅፋቶች ካጋጠሙ እንደዚሁም ሞት ከመጣ ግን መፋታት ይፈቀዳል፡፡ ቢኾንም በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ከተደነገገው ምክንያት በቀር መፋታት አይገባም (ፍት. ነገ. አን. ፳፬፣ ቍ. ፲፩-፲፯)፡፡

የጋብቻን ሕይወት ከሚፈታተኑ፣ የሩካቤ ሥጋ ሥርዓትን ከሚያዛቡ ተግባራት መካከል ዝሙት ዋነኛው ነው፡፡ ከፍተኛ የኾነ የሩካቤ ሥጋ ጥማት ወይም ሴሰኝነት ዝሙት ይባላል፡፡ ይኸውም ከጋብቻ ውጪ ሩካቤ ማድረግን፣ ግብረ ሰዶምንና በገዛ ሰውነት ላይ ፍትወተ ሥጋን መፈጸምን ያጠቃልላል፡፡ በሥልጣኔና በሌሎችም ሰይጣናዊ ተፅዕኖዎች የተነሣ በዓለማችን እየተለመደ የመጣው የዝሙት ኀጢአት ማለትም የተመሳሳይ ፆታ ጋብቻ፤ የወንዶች ከአንድ በላይ ሴት፣ የሴቶች ደግሞ ከአንድ በላይ ወንድ የማግባት ልማድ፣ ካገኙት ዂሉ ጋር በሩካቤ የመተዋወቅና የመሳሰለው አስነዋሪ ድርጊት ሊወገዝ ይገባል፡፡

ባለፉት ክፍሎች ለመዳሰስ እንደ ሞከርነው ሩካቤ ሥጋ፣ በጥንቃቄና በሥርዓት የሚፈጸም ግንኙነት ነው፡፡ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን መሠረት ጋብቻቸውን የፈጸሙ ሕጋውያን ሩካቤ የሚያደርጉበት ቀንና ሥርዓት ተወስኖላቸዋል፡፡ ለባለ ትዳሮቹ የሩካቤ ሥርዓት ከተሠራ ያለ ጋብቻ ከተገኘው ዂሉ ጋር መተኛት ምን ያህል የእግዚአብሔርን ሕግ መተላለፍ እንደ ኾነ ለመረዳት አያዳግትም፡፡ ከተመሳሳይ ፆታ ጋር ስለሚደረገው ግንኙነትስ (ግብረ ሰዶም) ይህ ነው ብሎ ለመናገር ይከብዳል፡፡ ምክንያቱም እንደ አስፈላጊነቱ እንጠቀምበት ዘንድ የተሰጠንን የተፈጥሮ ሕግ መጣስ፤ የሰውነት ክፍሎቻችንንም ማርከስ ነውና፡፡

እያንዳንዱ የሰውነት ክፍል የሥራ ድርሻ አለው፤ አንዱ ሕዋስ የሌላዉን ሥራ ማከናወን አይችልም፡፡ በፆታ ደረጃ ለወንድና ለሴት ለተመሳሳይ አገልግሎት የተሰጡን ሕዋሳት እንዳሉን ዂሉ ለወንዶች ብቻ ወይም ለሴቶች ብቻ የተሰጡ የአካል ክፍሎችም አሉ፡፡ ለሩካቤ ሥጋም ራሱን የቻለ ሕዋስ ተሰጥቶናል፡፡ ይህን የሰውነት ክፍል በጋብቻ ተወስነን ፈቃዳችንን በሥርዓት እንፈጽምበታለን፡፡ ነገር ግን ከዚህ በተለየ ዂኔታ ከተመሳሳይ ፆታ ጋር መገናኘት የእግዚአብሔርን ሥራ ከማንቋሸሽ ባለፈ ርኵሰትም ነው፡፡ ደግሞም ከእንስሳት ማነስ ነው፡፡ ማሰብና ማመዛዘን የማይችሉ እንስሳት እንኳን ከየትኛው ፆታ ጋር መገናኘት እንደሚገባቸው ይገነዘባሉ፡፡ እንስሳት የማያደርጉትን ይህን የረከሰ ተግባር መፈጸም ነባቢት፣ ሕያዊትና ለባዊት ነፍስ ካለችው፤ በዚያውም ላይ በእግዚአብሔር አርአያና ምሳሌ ከተፈጠረ የሰው ልጅ የማይጠበቅ አስነዋሪ ድርጊት ነው፡፡

ግብረ ሰዶም ከኀጢአት ዂሉ የከፋ ኀጢአት ነው፡፡ የኀጢአት ደመወዙ ደግሞ ሞት ነው፡፡ በምድር የነፍስና የሥጋ መለየት፣ በሰማይ ደግሞ በሲዖል (በገሃነመ እሳት) መጣል ሞት ይባላል፡፡ ግብረ ሰዶምን የሚፈጽሙ ሰዎችም ከተፈጥሮ ሥርዓት ውጪ በመጓዝ ከእንስሳት በታች ኾነዋልና ፍጻሜያቸው ሞት፤ የሞት ሞት ነው፡፡ ወይስ ዓመፀኞች የእግዚአብሔርን መንግሥት እንዳይወርሱ አታውቁምን? አትሳቱ፤ ሴሰኞች ቢኾን ወይም ጣዖትን የሚያመልኩ ወይም አመንዝሮች ወይም ቀላጮች ወይም ከወንድ ጋር ዝሙት የሚሠሩ፣ ወይም ሌቦች ወይም ገንዘብን የሚመኙ ወይም ሰካሮች ወይም ተሳዳቢዎች ወይም ነጣቂዎች የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም፤ እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ (፩ኛ ቆሮ. ፮፥፱-፲)፡፡

በብሉይ ኪዳን ከተመሳሳይ ፆታ ጋር ግንኙነት ሲፈጽሙ የነበሩ ሰዶማውያን ንስሓ ባለመግባታቸው ምክንያት በእሳትና በዲን ተቀጥተዋል፡፡ በዚህ ዘመን የተነሡ ሰዶማውያንም በምድር በመቅሠፍት፤ በሰማይም በገሃነመ እሳት መቀጣታቸው አይቀርም፡፡ ምክንያቱም ቅዱሱን የእግዚአብሔር ሰውነት አርክሰዋልና፡፡ በዚህ የርኵሰት ኀጢአት የሚገኙ ወገኖቻችን ከመጥፋታቸው በፊት በመምከርና በማስተማር ክርስቲያኖች ከኾኑ ለንስሓ እንዲበቁ፤ ሃይማኖት ከሌላቸውም ብንችል አስተምረን ማስጠመቅ፤ ባንችል ደግሞ የሚሠሩት ሥራ ከሰው የማይጠበቅ ተግባር መኾኑን ማስገንዝብ ይገባል፡፡ ሐዋርያው ይሁዳ እንዲሁም እንደ እነርሱ ዝሙትን ያደረጉና ሌላን ሥጋ የተከተሉ ሰዶምና ገሞራ በዙሪያቸውም የነበሩ ከተማዎች በዘላለም እሳት እየተቀጡ ምሳሌ ኾነዋል፤  በማለት ሰዶምና ገሞራ መጥፋታቸውን መጥቀሱ ግብረ ሰዶም የሚያመጣውን  መሪር ቅጣት በመገንዘብ ይህን ኀጢአት እንድንጸየፈውና እንድንርቀው ለማስተማር ነው (ይሁዳ. ፩፥፯)፡፡

የጽድቅ ሥራ እና የኀጢአት ተግባር በአንድ ልብ አመንጪነት ይፈጸማሉ፡፡ ልዩነቱ ጻድቃን ልቡናቸውን መልካም ነገርን ሲያሳስቡት፤  ኃጥኣን ደግሞ ለክፉ ነገር ማዋላችን ነው፡፡ “ደግ ሰው ከመልካም ልቡ መዝገብ መልካም ነገርን ያወጣል፤ ክፉ ሰው ግን ከክፉ ልቡ መዝብ ክፉ ነገርን ያወጣል፤” እንዲል (ማቴ. ፲፪፥፴፭)፡፡ በዚህ ዓለም እግዚአብሔርን የሚያስረሱን ሥጋውያን ተግባራት ብዙ ቢኾኑም፣ በአንጻሩ ደግሞ ፈቃደ ሥጋችንን በማሸነፍ ሕግጋቱን ጠብቀን ለመኖር የምንችልባቸው አጋጣሚዎችም አሉ፡፡ ጣዖት በሚመለክበት አካባቢ ቤተ ክርስቲያን እናገኛለን፤ ዓለማዊ ጫጫታ በሚበዛበት ቦታ ቅዳሴ እንሰማለን፡፡ እንግዲህ ለሥጋችን ነጻነት፣ ለነፍሳችን ድኅነት የሚጠቅመንን መምረጥ የእኛ ድርሻ ነው፡፡ ስለኾነም እሺ ብትሉ፣ ለእኔም ብትታዘዙ የምድርን በረከት ትበላላችሁ እንደ ተባልነው (ኢሳ. ፩፥፲፱) እንደ ዝሙት ያሉ አስነዋሪ ተግባራትን ከሚያስፈጽመን ሰይጣን ሸሽተን ቅዱሱን የእግዚአብሔርን መንፈስ ልንከተል ይገባናል፡፡

በአጠቃላይ መላው ምእመናን በተለይ እሳታዊ ባሕርይ የሚበረታብን ወጣቶች በምድር በልዩ ልዩ ደዌያት እንዳንያዝ፣ በሰማይም በገሃነመ እሳት እንዳንጣል ከዝሙት ሥራ ዂሉ ራሳችንን በመጠበቅ በተቀደሰው ጋብቻ ልንወሰን ያስፈልገናል፡፡ ከዝሙት ኀጢአት ነጻ ለመኾንም ፈሪሃ እግዚአብሔርን ገንዘብ ማድረግ፤ ሥጋን በጸሎት፣ በጾምና በስግደት እንደዚሁም በሥራ ማድከም፤ በስሜት አለመነዳት፤ ራስን ከስሜታዊነት መጠበቅ፤ ከዚህም ባሻገር ሞተ ወልደ እግዚአብሔርንና የቅዱሳንን ተጋድሎ ማስታወስ ዋነኛ መፍትሔዎች ናቸው፡፡

ስናውቅ በድፍረት፣ ሳናውቅ በስሕተት በሠራነው ኃጢአት እግዚአብሔር ይቅር እንዲለን ንስሓ ልንገባ ያስፈልጋል፡፡ እንደዚሁም እስመ ፍትወት ይእቲ እሞን ለኃሣራት ወለድካማት ወፃማት ወኃሣር ወበአማን ወላዲተ ሕማም ይእቲ ለሥጋውያን ወለመንፈሳውያን እስመ ይእቲ ታተልዎን ለመፍቅዳት ብዙኃት እለ ኢይትፈቀዳ ወትሬስዮን ከመ ዘይትፈቀዳ፤ የፈቲው ፆር የኃሣረ ሥጋ፣ የኃሣረ ነፍስ፣ የድካመ ሥጋ፣ የድካመ ነፍስ፣ የፃማ ሥጋ፣ የፃማ ነፍስ መገኛ ናት፡፡ ለሥጋውያንም ለመንፈሳውያንም መከራ ሥጋ መከራ ነፍስን የምታመጣ ናት፡፡ የማይወደዱ ብዙዎችን ፈቃዳት እንደሚወደዱ አድርጋ ታሳያለችና  እንደ ተባለው አምላካችን በዝሙት ከመውደቅ እንዲጠብቀን በጾም በጸሎት ልንተጋ ይገባናል፡፡

… ወንስአሎ ለእግዚአብሔር ተሰናዕዎ ወረድኤተ ወኃይለ ወምሕረተ …፤ የፈቲው ፆር የሚጸናብን አራቱ ባሕርያት ባይስማሙልን፤ አለመስማማታቸውም እግዚአብሔር ባይረዳን፤ አለመርዳቱም ኃይሉን ባያሳድርብን፤ ኃይሉን አለማሳደሩም ይቅር ባይለን ነውናይቅር በለን፤ ኃይልህን አሳድርብን፤ ርዳን፤ አራቱን ባሕርያት አስማማልንብለን እግዚአብሔርን ዘወትር እንለምነው” ተብሎ እንደ ተጻፈው በጸሎት ኃይል የሠለጠነብንን ዝሙት ድል ማድረግ ይቻለናልና (ፍት. ነገ. አን. ፳፬፣ ቍ. ፹፯-፹፰)፡፡

አምላከ ቅዱሳን እግዚአብሔር፣ በስሕተት ወይም በድፍረት የሠራነውን ዂሉ ኀጢአት ይቅር ብሎ፣ ለወደፊቱም ከኀጢአት ጠብቆ ዂላችንንም የመንግሥቱ ወራሾች ለመኾን ያብቃን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የጋብቻ ሕይወት እና የሩካቤ ሥርዓት – ክፍል ፱

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ፲፱ ቀን ፳፻፲ .

፪. የሩካቤ ሥጋ ሥርዓት

በባልና በሚስት መካከል የሚደረግ የመኝታ ግንኙነት ወይም መተዋወቅ ‹ሩካቤ ሥጋ፣ ግብረ ሥጋ› ይባላል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ሩካቤ ሥጋ ለአዳም የተሰጠውን ተስፋ ተከትሎ የመጣ ሥርዓት መኾኑን ይናገራሉ፡፡ ጥንተ ታሪኩም እንዲህ ነው፤ አዳምና ሔዋን ሕገ እግዚአብሔርን ጥሰው ከገነት ከወጡ በኋላ ጥረው ግረው በምድር እንዲኖሩ ተፈርዶባቸዋል፡፡ በዚህ ጊዜ አዳም እግዚአብሔርን “የሥጋዬን ነገርስ ነገርኸኝ፤ የነፍሴ ነገርስ እንደምን ይኾን?” ብሎ ጠየቀው፡፡ እግዚአብሔርም ይቅር ባይና ሰውን ወዳድ አምላክ ነውና ከአምስት ቀን ተኩል (አምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን) በኋላ ከሰማየ ሰማያት ወርዶ፣ ከልጅ ልጁ፣ (ከድንግል ማርያም) ተወልዶ፣ በፈቃዱ ተገፍፎ፣ ተገርፎ፣ በመስቀል ተሰቅሎ፣ ሥጋዉን ቆርሶ፣ ደሙን አፍስሶ፣ ሞቶ፣ ተነሥቶ እንደሚያድነው ቃል ኪዳን ገብቶለታል፡፡

የተስፋው ቃል እስከሚፈጸም ድረስ፣ አዳምና ሔዋን በሞተ ሥጋ ሞተ ነፍስ፣ በርደተ መቃብር ርደተ ገሃነም ተፈርዶባቸው በማዘንና በመተከዝ እያለቀሱ ይኖሩ ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ እግዚአብሔር አምላካችን አዳምን “አእምራ ለሔዋን፤ ሔዋንን በግብረ ሥጋ ዕወቃት” በማለት እንዲበዙ፣ እንዲባዙና ምድርን እንዲሞሏት አዘዛቸው (ዘፍ. ፫፥፲፯)፡፡ “ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ” የሚለው የተስፋው ቃል ይፈጸም ዘንድ ሩካቤ ሥጋ መፈጸም አስፈላጊ ነበረና አዳም ሔዋንን በግብር አውቋታል፡፡ “አዳምም ሚስቱን ሔዋንን አወቀ፤ ፀነሰችም፤ ቃየንንም ወለደች” እንዲል (ዘፍ. ፬፥፩፣ አንድምታ ትርጓሜ)፡፡

ከዚህ ታሪክ እንደምረዳው ሩካቤ ሥጋ፣ በአንድ በኩል ፈቃደ ሥጋን ለመቋቋም፤ በሌላ በኩል ደግሞ ለዘር መብዛትና ለትውልድ መቀጠል የሚያስፈልግ፤ በጋብቻ ለሚኖሩ ለሰው ልጆች የተሠራ ሥርዓት ነው፡፡ ከዚህ ባሻገር እግዚአብሔር አምላካችን ወንድና ሴትን ያስተሳሰረበት ማለት እንዲፈላለጉ ያደረገበት የድንቅ ጥበቡ መገለጫም ነው፡፡ ሁለቱን የጋብቻ ዓላማዎች ማለትም መረዳዳትንና ዘርን መተካትን የሚያስተሳስራቸውም ሩካቤ ሥጋ ነው፡፡ ባልና ሚስት በሩካቤ ወቅት የሚያገኙት የደስታ ስሜት እርስበርስ እንዲፈላለጉ የመሳሳቢያ መንገድ ይኾናቸዋል፤ የጋብቻ ሕይወታቸዉንም የጣፈጠ ያደርግላቸዋል፡፡ የሩካቤ ሥጋ ስሜት ባይኖር ኖሮ ሴትና ወንድ ላይፈላለጉ ይችሉ ነበር፡፡ ምክንያቱም ፈቃድን ለመፈጸም ካልተቻለ ልጅ ለመውለድ ብቻ ወይም ለመረዳዳት ብሎ ወደ ጋብቻ ሕይወት የሚገባ ሰው ለማግኘት ይከብዳልና፡፡

ስለዚህም የሰው ልጅ መጋባትን እንዳይጠላ እግዚአብሔር አምላክ ሴትና ወንድ የሚፈላለጉበትን ስሜት (ሩካቤ ሥጋን) ፈጥሯል፡፡ ኾኖም ግንኙነቱ ሥርዓት ባለውና በሕጋዊ መንገድ እንጂ እንደ እንስሳት በዘፈቀደ አይፈጸምም፡፡ አዳምና ሔዋን በሩካቤ ሥጋ የተዋወቁት ከገነት ወጥተው ቆይተው ንስሓ ከገቡ በኋላ መኾኑም ሩካቤ ሥጋ ጥንቃቄ የሚያስፈልገው ግንኙነት መኾኑን ያመለክታል፡፡ ከጋብቻ ውጪ ሩካቤ ሥጋ መፈጸም እንደማይቻልም ቤተ ክርስቲያናችን በአጽንዖት ታስተምራለች፡፡ በጋብቻ እስካልተወሰንን ድረስ ካገኘነው ዂሉ ጋር መተኛት ሕገ እግዚአብሔርን መጣስ፣ ሰውነትን ማርከስ ነውና፡፡ ከዚህም ባለፈ ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚያመጣብን ቅጣትም የከፋ መኾኑን መረዳት ይኖርብናል፡፡

በመኾኑም ያላገባን እስክናገባ ድረስ ክብራችንን መጠበቅ፤ በጋብቻ የተወሰንን ሰዎችም እስከ መጨረሻው ድረስ ተዋሕዷችንን ማጥበቅ ይገባናል፡፡ ስለ ተጋባን ብቻ ከሥርዓት ውጪ ሩካቤ ሥጋን መፈጸም እንደማይገባም መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ እያንዳንዱ ቀን የሥራ፣ የጸሎት፣ የጾምና የመመገቢያ (የደስታ) ሰዓት እንዳለው ዂሉ ሩካቤን ለመፈጸምም የተወሰነ ሥርዓት አለው፡፡ በቂ የሕሊና ዝግጅትና ስምምነትም ያስፈልገዋል፡፡ በጋብቻ ግንኙነት የሚወለዱ ሕፃናት የተባረኩና የተቀደሱ ይኾኑ ዘንድ መኝታው ንጹሕ ሊኾን ይገባዋልና፡፡ “ጋብቻ ክቡር፣ መኝታውም ንጹሕ ይኹን፤ ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል” እንዳለ (ዕብ. ፲፫፥፬)፡፡ ሩካቤ ሥጋን ሥርዓት በሌለው መንገድ መፈጸም የጋብቻን ክቡርነት፣ የመኝታውንም ንጽሕና ማቃለል ነው፡፡

፪.፩ ሩካቤ ሥጋ የማይፈጸምባቸው ጊዜያት

ሩካቤ ሥጋ፣ በምን ዓይነት ሥርዓት ሊፈጸም እንደሚገባው በሕገ ቤተ ክርስቲያን እንዲህ ተደነግጓል፤ “ወሰብሳብሰ ዘሠርዖ እግዚአብሔር ለደቂቀ ዕጓለ እመሕያው አኮ በእንተ ወሊደ ውሉድ ባሕቲቱ አላ በእንተ መፍቅድ ዘኢዕቁብ ወባሕቱ ኢይኩን በርኵስ፤ እግዚአብሔር ሩካቤን ለሰው የሠራው ልጅ ለመውለድ ብቻ አይደለም፤ የማይወሰን የማይገታ የፈቲውን ፆር ለማራቅ ጭምር ነው እንጂ፡፡ አንድ ጊዜ የሚከለከሉበትን፣ አንድ ጊዜ ፈቃዳቸውን የሚፈጽሙበትን ሠራ፡፡ ነገር ግን አንድ ወንድ ለአንድ ሴት፣ አንዲት ሴት ለአንድ ወንድ ብለው ዘወትር ሊያደርጉት አይገባም፡፡ አጽዋማትን፣ በዓላትን፣ ኅርስን፣ ትክትን ለይቶ ሊያደርጉት ይገባል እንጂ፤” (ፍት. ነገ. አን. ፲፭፥፣ ቍ. ፴፰-፵፰)፡፡ ከላይ እንደ ገለጽነው ሩካቤ ሥጋ በሥርዓት የሚፈጸም እንደ መኾኑ የማይፈጽምባቸው ጊዜያትም አሉ፡፡ እነዚህም የሚከተሉት ናው፤

ሀ. የእርግዝና እና የንጽሕ ጊዜያት

ሚስት በፀነሰችበት ወይም ባረገዘችበት ወቅት፤ በወር አበባዋና በመውለጃዋ ጊዜ (ወንድ ከወለደች ከዐርባ፣ ሴት ከወለደች ከሰማንያ ቀን በፊት) ሩካቤ ሥጋ መፈጸም አይገባም (ዘሌ. ፳፥፲፰)፡፡ ቅዱስ ባስልዮስም “ወበመዋዕለ ትክቶሃ ወኅርሳ ኢትቅረባ ከመ ኢይኩን ተዋስቦትከ ዘእንበለ ሕግ፤ በኅርሷ፣ በደሟ ወራት ሚስትህን አትድረስባት፡፡ ግቢህ ከመጽሐፍ ሥርዓት የወጣ እንዳይኾን” በማለት በፅንስ (እርግዝና) እና በንጽሕ ጊዜያት ማለትም በአራስነትና በወር አበባ ወቅት ግንኙነት መፈጸም እንደማይገባ አዝዟል (ፍት. ነገ. አን. ፳፬፣ ቍ. ፷፬)፡፡ በተመሳሳይ መልኩ የሚስት ፅንሷ ከታወቀ በኋላ ለመረዳዳት ካልኾነ በቀር ባሏ ሊቀርባት እንደማይገባ ተደንግጓል (አን. ፳፬፣ ቍ. ፰፻፴፰)፡፡

ለ. ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚሔዱባቸው ቀናት

እስራኤላውያን እግዚአብሔር ከሙሴ ጋር ሲነጋገር ከመስማታቸው (ሕጉን ከመቀበላቸው) ከሦስተኛው ቀን በፊት እንዲቀደሱ፣ ልብሳቸውን እንዲያጥቡና ሩካቤ እንዳይፈጽሙ ታዝዘው ነበር፡፡ ዛሬም በሐዲስ ኪዳን ባለ ትዳሮች ትምህርተ ወንጌል ለማዳመጥ፣ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለመቀበል፣ ጠበል ለመጠመቅና ለመጠጣት፣ ወይም ለሌላ አገልግሎት ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲሔዱ ከሩካቤ ሥጋ እንዲከለከሉ ታዝዟል (ዘፀ. ፲፱፥፲-፳፭)፡፡ ከዚህም ሌላ በጥምቀት ክርስትና የሚያነሡ (የክርስትና እናት ወይም አባት የሚኾኑ ምእመናን) ክርስትና ከማንሣታቸው በፊትና በኋላ ለሁለት ቀናት ከሩካቤ ሥጋ መከልከል ይገባቸዋል፡፡ ይኸውም መንፈስ ቅዱስን ለማክበር ነው፡፡ ምሥጢረ ጥምቀት ጸጋን፣ ክብርንና ልጅነትን የሚያሰጥ ምሥጢር ስለ ኾነ፡፡ ካህኑ ዘካርያስ የቤተ መቅደሱን አገልግሎት ከፈጸመ ከሁለት ቀን በኋላ ከኤልሳቤጥ ጋር መገናኘቱም ለዚህ ትምህርት ነው፡፡ “ወእምድኅረ ክልኤ መዋዕል ፀንሰት ኤልሳቤጥ ብእሲቱ፤ ከሁለት ቀን በኋላም ሚስቱ ኤልሳቤጥ ፀነሰች” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሉቃ. ፩፥፳፬፤ ፍት. ነገ. አን. ፳፬፣ ቍ. ፴፰)፡፡

ሐ. በዓላት

ቅዳሜ፣ እሑድና በዓበይት በዓላት ሩካቤ ሥጋ መፈጸም የተከለከለ ነው፡፡ ይኸውም በመንግሥተ ሰማያት ጋብቻና ፈቃደ ሥጋን መፈጸም አለመኖሩን ለማጠየቅ ነው፡፡ በዓላት፣ የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌዎች ናቸውና ፡፡ “በትንሣኤስ እንደ እግዚአብሔር መላእክት በሰማይ ይኾናሉ እንጂ አያገቡም አይጋቡምም” እንዲል (ማቴ. ፳፪፥፴)፡፡ ሌላው ምክንያት ደግሞ “ንጹሕ የኾነ ነውርም የሌለበት አምልኮ በእግዚአብሔር አብ ዘንድ ይህ ነው … በዓለምም ከሚገኝ እድፍ ሰውነቱን መጠበቅ ነው” በማለት ቅዱስ ያዕቆብ እንደ ተናገረው (ያዕ. ፩፥፳፯)፣ በእነዚህ ዕለታት ወደ ቤተ ክርስቲያን በመሔድ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን መቀበልና ራስን መጠበቅ ተገቢ ስለ ኾነ ነው፡፡ “ፈቃድህን በተቀደሰው ቀኔ ከማድረግ እግርህን ከሰንበት ብትመልስ፣ ሰንበትንም ደስታ፣ እግዚአብሔርም የቀደሰውን ‹ክቡር› ብትለው፣ የገዛ መንገድህንም ከማድረግ፣ ፈቃድህንም ከማግኘት፣ ከንቱ ነገርንም ከመናገር ተከልክለህ ብታከብረው፣ በዚያን ጊዜ በእግዚአብሔር ደስ ይልሃል፤ በምድርም ከፍታዎች ላይ አወጣሃለሁ፤ የአባትህንም የያዕቆብን ርስት አበላሃለሁ” ተብሎ ተጽፏልና (ኢሳ. ፶፰፥፲፫-፲፬)፡፡

መ. አጽዋማት

“ጸዋሚ ሆይ፥ መላው አካልህ ይጹም፤ አፍህ ክፉ ከመናገር፣ አንደበትህ ከሐሜትና ከስድብ፣ ዓይንህ ሴቶችን ከማየት፣ ጆሮህም ዘፈንና ጨዋታ ከመስማት ይጹም” ተብሎ እንደተ ነገረን (ርቱዐ ሃይማኖት) ሩካቤ ሥጋም ሰውነት የሚደሰትበት ፈቃድ ስለ ኾነ በጾም ወቅት መታቀብ ይገባል፡፡ “ወመፍቅደ ሕግሰ በጾም ከመ ትድክም ኃይለ ፍትወት … ወዓዲ ከመ ያምልኮ ለእግዚአብሔር በኵለንታሁ በአሠንዮተ ጾም እመንገለ ተአንስሶ ወበጸሎት እመንገለ ነባብያን፤ ጾምን ያሻው ፈቃድ የፈቲው ፆር ትደክም ዘንድ ነውና … ዳግመኛም ሰው እንስሳትን በሚመስልበት ባሕርዩ በጾም፤ መላእክትን በሚመስልበት ባሕርዩ በጸሎት እግዚአብሔርን በነፍስ በሥጋው ያገለግል ዘንድ ነው” ተብሎ ተጽፏል (ፍት. ነገ. ፲፭)፡፡ ስለዚህም በጾም ጊዜያት ሩካቤ ሥጋ ከመፈጸም መታቀብ ያስፈልጋል፡፡ “ኢታርስሖን ለመዋዕላት ቅዱሳት እንተ ጾም፤ ጾም የሚጾምባቸውን ዕለታት አታሳድፋቸው” እንዳለ ቅዱስ ባስልዮስ፡፡

ይኸውም ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ ለማስገዛትና የሚወለዱ ልጆችን ከደዌ ለመጠበቅ ሲባል የተሠራ ሕግ ነው፡፡ “በጾም ወቅት ከሩካቤ መከልከል ስለ ጾም የሚኾን ፈቃደ ነፍስ ይፈጸም ዘንድ ነው፡፡ ይኸውም ነባቢት ነፍስን ለማክበር ደማዊት ነፍስን ከእንስሳዊ ግብር መከልከል ነው፡፡ ሰውነትን (ሥጋ) በሚጐዳ በጾም ወራት ሰውነቱን፣ ልጁን ከደዌ ለመጠበቅ ለሰው ዂሉ እያንዳንዱ ከሩካቤ መከልከል ይገባዋል” እንዲል (ፍት. ነገ. አን. ፳፭፥፣ ቍ. ፶-፶፪)፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ባልና ሚስት በንስሓ አባታቸው የተሰጣቸዉን የንስሐ ቀኖና ወይም በራሳቸው ፈቃድ የገቡትን የጾም ሱባዔ እስከሚፈጽሙ ድረስ ከሩካቤ ሥጋ መከልከል ይገባቸዋል፡፡

በአጠቃላይ ባልና ሚስት በፅንስ፣ በአራስነትና በወር አበባ ወቅት፤ እንደዚሁም በበዓላትና በአጽዋማት ቀን ሩካቤ ሥጋ ማድረግ እንደማይገባቸው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታስተምራለች፡፡ ከዚህ በተረፈ ግን ሰይጣን የሚፈትንበትን ክፍተት እንዳያገኝ ባልና ሚስት ሊለያዩ አይገባም፡፡ “ለጸሎት ትተጉ ዘንድ ተስማምታችሁ ለጊዜው ካልኾነ በቀር እርስ በርሳችሁ አትከላከሉ፤ ራሳችሁን ስለ አለመግዛት ሰይጣን እንዳይፈታተናችሁ ደግሞ አብራችሁ ኹኑ፤” እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ (፩ኛ ቆሮ. ፯፥፭)፡፡ ይህ የሐዋርያው ትምህርት “ሰውነታችሁን ንጹሕ አድርጋችሁ በምትጾሙበት፣ በምትጸልዩበት ጊዜ ነው እንጂ ሥራችሁን ከፈጸማችሁ በኋላ ግን ወደ ፈቃዳችሁ ተመለሱ፡፡ የምትሹትን ስላጣችሁ ሰይጣን ድል እንዳይነሳችሁ” ተብሎ በፍትሐ ነገሥትም ተጠቅሷል (አን. ፲፭፣ ቍ. ፳፬)፡፡ ይህም ባልና ሚስት፣ የጾም፣ የጸሎት፣ የበዓል ወቅት ካልኾነ በቀር ሳይለያዩ ፈቃዳቸዉን መፈጸም እንደሚገባቸው ያስገነዝባል፡፡

ይቆየን

የጋብቻ ሕይወት እና የሩካቤ ሥርዓት – ክፍል ፰

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ፲፰ ቀን ፳፻፲ .

ለ. ምንኵስና

ምንኵስና፣ ‹መንኰሰ – ሞተ› ካለው የግእዝ ግስ የተገኘ ቃል ሲኾን ትርጓሜውም ሥጋዊ ስሜትን መግደልን (ማሸነፍን) ያመላክታል፡፡ ይኸውም ሥጋዊ ስሜትን በመግታት ራስን የመንፈስ ደሃ ማድረግን፤ ምድራዊ ደስታን በመናቅ ለሰማያዊው መንግሥት መዘጋጀትን የሚያጠይቅ ነው፡፡ ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ብልና ዝገት በሚያጠፉት፣ ሌቦችም ቆፍረው በሚሠርቁት ዘንድ ለእናንተ በምድር ላይ መዝገብ አትሰብስቡ፡፡ ነገር ግን ብልም ዝገትም በማያጠፉት ሌቦችም ቆፍረው በማይሠርቁት ዘንድ ለእናንተ በሰማይ መዝገብ ሰብስቡ፤” በማለት ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ ማስገዛት ሰማያዊ ዋጋ እንደሚያስገኝ ተናግሯል (ማቴ. ፮፥፲፱-፳)፡፡ ምንኵስና፣ ጌታችን የሰጠውን ይህን ተስፋ መሠረት በማድረግ አባቶችና እናቶች በብሕትውና (በብቸኝነት) የሚኖሩበት ሕይወት ሲኾን፣ ይኸውም ምድራዊውን ተድላና ደስታ የሚያስተው፤ ከሥጋ ጥቅም ይልቅ ለነፍስ የሚያደላ የቅድስና ኑሮ ነው፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት ምንኵስና፣ ቍምስናንና ጵጵስናን የመሰሉ የክህነት መዓርጋትን ለመቀበል አንደኛው መሥፈርት ነው፡፡ ስለዚህም አንድ ዲያቆን በሕግ ተወስኖ (ሚስት አግብቶ) መኖር ካልፈለገና በቍምስና ወይም በኤጲስ ቆጶስነት ከፍ ሲልም በጵጵስና የማገልገል ዓላማ ካለው ቅስና ከመቀበሉ አስቀድሞ መመንኰስ ግድ ይለዋል፡፡ ሚስት ማግባትን ከመረጠ ግን ከቅስና መዓርግ ባለፈ ለኤጲስ ቆጶስነትም ለጵጵስናም ሊበቃ አይችልም፡፡ ኾኖም ምንኵስና፣ ለደናግል ብቻ ሳይኾን ለመዓስባንም ማለትም ትዳር መሥርተው ለኖሩ ምእመናንም ይፈቀዳል፡፡ የተቻላቸው ከሴት ጋር ሳይተዋወቁ (ትዳር ሳይመሠርቱ) በድንግልናቸው እንደ ጸኑ ይመነኵሳሉ፡፡ ሌሎች ደግሞ ጋብቻ መሥርተው ከቆዩ በኋላ በሞት ወይም በሌላ ምክንያት ከትዳር አጋራቸዉ ጋር ቢለያዩ መመንኰስ ይችላሉ፡፡ በእርግጥ ይህ የሚኾነው ፈቃደ ሥጋቸዉን (የፍትወት ስሜታቸዉን) ለማሸነፍ ከቻሉ ብቻ ነው፡፡ ሁለተኛ የማግባት ፍላጎቱ ያላቸው ወገኖች ግን እንዲመነኵሱ አይገደዱም፡፡

ወደ መነሻ ርእሳችን ስንመለስ ፍቺ ከሚፈቀድባቸው መንገዶች አንደኛው ምንኵስና ነው፡፡ ይኸውም በፍትሐ ነገሥት እንደ ተገለጸው ባልና ሚስት “አይበላስ የለም፤ አይጠገብ ይባስ” ብለው በፈቃዳቸው ለመመንኰስ ሲወስኑ ነው፡፡ ውሳኔው ግን የሥጋ ስሜትንና የቤተሰብ ኹኔታን ባገናዘበ መልኩ መኾን አለበት፡፡ ምክንያቱም አንዳቸው ለመመንኰስ ፈልገው አንዳቸው ፈቃደኛ ካልኾኑ ወይም ልጆችን የሚረከብና የሚያሳድግ ሰው ከሌለ ቤተሰብን በትኖ መመንኰስ ተገቢ አይደለምና፡፡ ሁለቱም ጥንዶች ፈቃደ ሥጋ ጠፍቶላቸው ከኾነ፣ ልጆቻቸዉን የሚያሳድግላቸውም ከተገኘ (ወልደው ከኾነ) ተመካክረው መመንኰስና መለያየት ይችላሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ጋብቻ ይፈርሳል (ፍቺ ይፈቀዳል)፡፡ ከዚህ ላይ ልናስተውለው የሚገባን ቁም ነገር ከመነኰሱ በኋላ ወደ ጋብቻ መመለስ በፍጹም አይፈቀድም፡፡ ስለዚህም ያላገባንም ኾነ ያገባን ሰዎች በስሜታዊነት ተነሣሥተን ፈቃደ ሥጋችንን በትክክል ሳናዳምጥ መመንኰስ የለብንም፡፡ የምንኵስና ሕይወት ከገቡ የማይወጡበት የመላእክት ሥርዓት ነውና፡፡

ሐ. ሞት

መፋታት የሚፈቀድበት ሌላኛውና ዋነኛው መንገድ ሞት ነው፡፡ ሞት ለሰው ልጅ የማይቀር ጥሪ ነውና ባልና ሚስት ተስማምተው እየኖሩ ሳሉ ከሁለት አንዳቸው በሞት ሊለዩ ይችላሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ሁለተኛ ጋብቻ (ፍቺ) ይፈቀዳል፡፡ በሕይወት የቀረው ወገን ለብቻው መኖር ከተቻለው ራሱን ጠብቆ ቢኖር መልካም ነው። ፍትወትን መጠበቅ ካልተቻለ ግን ለሁለተኛ ወይሜ ለሦስተኛ ጊዜ ማግባት ይፈቀዳል፡፡ የትዳር አጋር በሞት ከተለየ በኋላ በሕይወት ያለው ወገን ከጋብቻ ሕግ ነጻ ነውና፡፡ ለዚህም ማስረጃ የሚኾነን የሚከተለው የቅዱስ ጳውሎስ ትምህርት ነው፤ “ያገባች ሴት ባልዋ በሕይወት ሲኖር ከእርሱ ጋር በሕግ ታስራለችና፤ ባልዋ ቢሞት ግን ስለ ባል ከኾነው ሕግ ተፈታለች፡፡ ስለዚህ ባልዋ በሕይወት ሳለ ለሌላ ወንድ ብትኾን አመንዝራ ትባላለች፤ ባልዋ ቢሞት ግን ከሕጉ አርነት ወጥታለችና ለሌላ ወንድ ብትኾን አመንዝራ አይደለችም … ሴት ባልዋ በሕይወት ሳለ የታሰረች ናት፤ ባልዋ ቢሞት ግን በጌታ ይኹን እንጂ የወደደችውን ልታገባ ነጻነት አላት” (ሮሜ. ፯፥፪፤ ፩ኛ ቆሮ. ፯፥፲፩-፴፱)፡፡

መ. ሌሎች መንገዶች

ከዝሙት፣ ከምንኵስና እና ከሞት በተጨማሪ በተፈጥሮ ወይም በድንገተኛ ምክንያት የመራቢያ አካላትን ጤንነት የሚያውክ ደዌ ወይም ሌላ ችግር ከተከሠተ ፍቺ እንደሚፈቀድ በሕገ ቤተ ክርስቲያን ተደንግጓል፡፡ ለምሳሌ የአባለ ዘርዕ መሰለብ ካጋጠመ፣ ሩካቤ ሥጋ መፈጸም ካልተቻለ ማለት የመራቢያ አካላት ለሩካቤ ሥጋ ብቁ ካልኾኑ ለአንደኛው ደኅነትና ደስታ ብሎም ሰላማዊ ሕይወት ሲባል መፋታት ይቻላል፡፡ ከዚሁ ዂሉ ጋርም አንዱ በሌላው ሕይወት ላይ ለሞት የሚያበቃ በደል ወይም ድብደባ በየጊዜው የሚፈጽም ከኾነ፤ ከዚህ ክፉ ልማድም በምክር ካልተመለሰ፤ እንደዚሁም አንደኛው ወገን ሃይማኖቱን ከለወጠና አልመለስም ካለ መፋታት ይፈቀዳል፡፡ ከዚህም ሌላ አንደኛው ወገን ባልታወቀ ምክንያት ከአገር ቢጠፋና ባይመለስ አንደኛው አካል ለአምስት ዓመታት ከጠበቀ በኋላ ሌላ ማግባት ይችላል፡፡

በተመሳሳይ መልኩ የዕድሜ ልክ ወይም የብዙ ዓመታት እስራት ቢፈረድበትና አንደኛው ወገን መታገሥ ካልቻለ ከንስሐ አባት ጋር ተመካክሮ ፍቺ መፈጸምና ሌላ ማግባት ይቻላል፡፡ እንደዚሁም አንደኛው አካል ወደ ውትድርና ሔዶ መሞቱ በምስክር ከተረጋገጠ፣ ከሞተ ከአንድ ዓመት በኋላ ያልሞተው ወገን ሌላ ትዳር መመሥረት ይችላል፡፡ ከላይ በተጠቀሱ ምክንያቶች መፋታትና ሁለተኛ ጋብቻን መመሥረት ቢቻልም ከመለያየት በፊት ችግሮችን በውይይት ለማስተካከልና ለመስማማት ከፍተኛ ጥረት ማድረግ እንደሚገባን መዘንጋት የለብንም፡፡ ምክንያቱም ‹‹መፋታት ይፈቀዳል›› በሚል ሰበብ በሚረባውም በማይረባውም ጉዳይ ጋብቻን ማፍረስ ተገቢ አይደለምና፡፡

ግጭት፣ ሐሜት፣ አሉባልታ፣ ጭቅጭቅ፣ ቅናት፣ ሱስና የመሳሰሉ ጎጂ ልማዶች ጋብቻን ከሚፈታተኑ ችግሮች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ እነዚህ ልማዶች የትዳር ሕይወትን አሰልቺ ሊያደርጉት ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ለፍቺ የሚያበቁ አይደሉም፡፡ ምክንያቱም በሁለቱ ጥንዶች መካከል ውስጣዊ መናበብ ካለ ለችግሮቹ መፍትሔ ማምጣት ይቻላልና፡፡ ለዚህም መፍትሔው ከጸሎት ቀጥሎ የችግሩን መንሥኤ በትክክል መረዳትና መውጫ መንገዱን መፈለግ ነው፡፡ በመሠረቱ በጋብቻ ሕይወት የሚያጋጥሙ መሰናክሎችን እንደ መልካም አጋጣሚ መውሰድ እንችላለን፡፡ እንዴት ከተባለ የትዳራችንን መሥመር ለማስተካከል በምናደርገው ጥረት ውስጥ ልዩ የፍቅር ጕዞ ልንጀምር ስለምንችል፡፡ ለምሳሌ ከጥንዶች አንዱ እያመሸ የሚገባ፣ በሱስ የተጠመደ፣ የሚጨቃጨቅ፣ የሚሳደብ፣ ወዘተ ከኾነ ከመቈጣትና ከማጥላላት ይልቅ ከዚህ ልማድ እንዲወጣ ልዩ ክብካቤ ማድረግ ውጤቱ ጥሩ ይኾናል፡፡ ይህም ትዳሩን ይበልጥ እንዲወድና ራሱን እንዲያይ ሊያግዘው ይችላል፡፡ ፍቅር፣ የጠብ ዂሉ መድኀኒት ናትና፡፡

በአጠቃላይ የመጀመሪያ ጋብቻን ማፍረስና ሁለተኛ ወይም ከዚያ በላይ ማግባት ባይፈቀድም ሃይማኖትን የሚያስክድ፣ ሩካቤ ሥጋን የሚከለክልና ለሕይወት የሚያሠጋ ይኸውም ሊቀረፍ የማይችል ችግርና ጭንቅ ከመጣ መፋታት ተፈቅዷል፡፡ ፍቺ የሚፈቀድባቸው መንገዶችም በፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፳፬፣ ከቍጥር ፱፻፵-፱፻፶፰ ተዘርዝረዋል፡፡ በዚህ መሠረት ጋብቻ እንደ አስፈላጊነቱና እንደ ኹኔታው እስከ ሦስት ጊዜ ድረስ ሊፈቀድ ይችላል፡፡ ከዚያ በላይ ግን እንደ ርኵሰት ይቈጠራል፡፡ ከላይ የተዘረዘሩትን የመሰለ ችግር ካልመጣ በቀር ቀላ (ቀላች)፤ ጠቈረ (ጠቈረች) ከሣ (ከሣች)፤ አጠረ (አጠረች)፤ ቀጠነ (ቀጠነች)፤ ደኸየ (ደኸየች) ብሎ ትዳርን ማፍረስ ተገቢ አለመኾኑን ቅዱሳት መጻሕፍት ያስተምራሉ፡፡ ሕመም ቢያጋጥም ማስታመም፣ ድህነት ቢመጣ አብሮ ማሸነፍ፣ ፈተና ቢበዛ በጋራ ድል ማድረግ እንጂ ትዳርን በየሰበቡ ማፍረስ ክርስቲያናዊ ምግባር አይደለምና፡፡

ይቆየን

የጋብቻ ሕይወት እና የሩካቤ ሥርዓት – ክፍል ፯

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ፲፯ ቀን ፳፻፲ .

፩.፰ ፍቺ የሚፈቀድባቸው መንገዶች

በክፍል ስድስት ዝግጅታችን እንደ ጠቀስነው ጋብቻ፣ ፈተና ቢበረታበትም መነጣጠል፣ መለያየት የማይስማማው ጥምረት ነው፡፡ ስለዚህም ‹‹ከዛሬ ጀምሮ በቃኝ›› ተብሎ የሚቋረጥ የኮንትራት ኑሮ አይደለም፡፡ ኾኖም ለጥንዶቹ ሰላማዊ ኑሮ፣ ለሕይወቱ ክብርና ለተጣመሩበት ሥጋ ወደሙ ቅድስና እንቅፋት የሚያመጡና በውይይት ወይም በእርቅ የማይስተካከሉ ችግሮች ከተከሠቱ መፋታት ይፈቀዳል፡፡ ሁለተኛ ጋብቻ መመሥረትም ይቻላል፡፡ ፍቺ መፈጸምና ሁለተኛ ጋብቻ መመሥረት ከሚቻልባቸው መንገዶች መካከል ዋና ዋናዎቹም የሚከተሉት ናቸው፤

ሀ. ዝሙት

መፋታት ከሚፈቀድባቸው መንገዶች መካከል አንደኛው ዝሙት ነው፡፡ ዝሙት፣ ያገቡትንም ያላገቡትንም የሚፈታተን የኀጢአት ዓይነት ነውና ስለዚህ ኀጢአት መጠነኛ ትምህርት ማቅረብ አስፈላጊ ነው፡፡

ወደ ትምህርቱ ስንገባ ከጋብቻ ውጪ የሚደረግ ማንኛውም ዓይነት ሩካቤ ሥጋ (አመንዝራ) ‹ዝሙት› ይባላል፡፡ ይህም በትዳር ላይ ሌላ ሴት (ወንድ) መደረብ ወይም መሰራረቅ (ከሌላ መሔድ) ነው፡፡ ሴሰኝነት ደግሞ ከፍተኛ የዝሙት ስሜትን ያመለክታል፡፡ ዝሙት፣ አመንዝራ፣ ሴሰኝነት ዂሉም ካልጠግብ ባይነትና ራስን ካለመግዛት የሚመጡ የኀጢአት ዘሮች ናቸው፡፡ የዝሙት መንፈስ የስስት ውጤትም ነው፤ ይኸውም ያለኝ ይበቃኛል አለማለትና ዐዲስ ነገርን ያውም የራስ ያልኾነን ነገር መመኘት ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን “የባልጀራህን ሚስት አትመኝ፡፡ የባልንጀራህንም ቤት እርሻዉንም ሎሌዉንም ገረዱንም በሬዉንም አህያዉንም፣ ከባልንጀራህ ገንዘብ ዂሉ ማናቸውንም አትመኝ፤” በማለት መፈጸም ይቅርና መመኘት እንኳን እንደማይገባን አዝዞናል (ዘፀ. ፪፥፲፯፤ ዘዳ. ፭፥፳፩)፡፡ ዝሙት ማለት እንግዲህ የእግዚአብሔርን ሕግ በመተላለፍ ከሚስት (ከባል) ውጪ በመሴሰን ሰውነትን ማቆሸሽ ነው፡፡

የእግዚአብሔር ቃል የሚናገረው ዐቂበ ርእስን (ራስን መጠበቅ) ገንዘብ ስለ ማድረግና በንጽሕና ስለ መጽናት ቢኾንም ቃሉን በተግባር የሚፈጽሙት ግን ጥቂቶች ናቸው፡፡ ዝሙትን ልማድ አድርገን የምንኖር ኀጥኣን በርካቶች ነን፡፡ ከዚህ ክፉ ልማድ የምንረዳውም ሰይጣን ወደ ምድር ከለቀቀብን የወረርሽኝ በሽታዎች መካከል ዝሙት ከፍተኛውን ቦታ እንደሚይዝ ነው፡፡ በልዩ ልዩ የዓለም ክፍሎች እንደምንሰማው አንድ ለአንድ መወሰንና ከጋብቻ በፊት ራስን መጠበቅ እንደ ኋላ ቀርነት የተቈጠረ ይመስላል፡፡ “ጓደኛ” በሚል ሰበብ አንድ ወንድ የብዙ ሴቶች ባል፤ አንዲት ሴት የብዙ ወንዶች ሚስት የሚኾኑበት አጋጣሚ ተለምዷል፡፡ በተለይ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በሚገኙባቸው አካባቢዎች ግብረ ዝሙት እየተስፋፋ ይገኛል፡፡ በስካር፣ በስሜታዊነት ወይም በግዴለሽነት ተገፋፍተን ካገኘነው ዂሉ ጋር በዝሙት የምንድቅ ወነኖች ቤት ይቍጠረን፡፡ ይህ ዂሉ ከዘማዊነታችን የመነጨ ውጤት ነው፡፡

ከጣልያን ወረራ ጊዜ ጀምሮ በአገራችን እንደ ተስፋፋ የሚነገርለት የሴተኛ አዳሪነት ልማድ ባለ ትዳሮችን ጨምሮ የበርካታ ወጣቶችን ሕይወት እየበከለ ይገኛል፡፡ በየመገናኛ ብዙኃኑ እንደምንሰማው ሕፃናትን ጨምሮ በርካታ ወጣት እኅቶቻችን ገንዘብ ለማግኘት በሚል ሰበብ ለከፍተኛ ችግር ተጋልጠዋል፡፡ ለሥነ ልቡናዊ ችግርና ለልዩ ልዩ በሽታ የሚጋለጡ እኅቶቻችን ጥቂቶች አይደሉም፡፡ ከዚሁ ዂሉ ጋርም ፅንስ ለማስወረድ በሚያደርጉት ጥረት የሚሞቱም ብዙዎች ናቸው፡፡ ከማያውቁት ወንድ የሚወልዱ እናቶችና አባታቸውን የማያውቁ ልጆችም እንዳሉም ለመገመት አያዳግትም፡፡ ይኼ ደግሞ በእናቶችም በልጆችም የሚያስከትለው የሥነ ልቡና ተጽዕኖ ቀላል አይደለም፡፡ የእግዚአብሔር አገር በምትባለው በኢትዮጵያ የምንኖር ክርስቲያኖች ሳይቀር የዚህ ኀጢአት ሰለባዎች መኾናችን እጅግ ያሳፍራል፤ ያሳዝናልም፡፡

በዝሙት መተዳደር ከሚያስገኘው ገንዘብና ከመብትነቱ ይልቅ ነጻነትን የሚቀማና ማንነትን የሚያሳጣ ተግባር መኾኑን በማስተዋል ይህን ድርጊት የሚከለክል ሕግ በአገራችን መንግሥት ሊወጣም ይገባል፡፡ መብት ማለት ለሰዎች የሚጠቅም ምርጫ እንጂ እየተጎዱ እንዲኖሩ መፍቀድ ማለት አይደለምና፡፡ በመኾኑም የዝሙት ተግባር ከመብትና ከገቢ ምንጭነት በተለየ መንገድ ቢታይ መልካም ነው፡፡ ወገኖቻችን በእንጀራ ምክንያት ራሳቸውንም ሌሎችንም ወደ ጥፋት እየወሰዱ ነውና፡፡

ጋብቻ የመሠረትን ትዳራችንን ወደ ኋላ በመተው፣ ያላገባንም ራሳችንን በመጣል ከማናውቃቸው ሴቶች ጋር ሰውነታችንን ማሳደፍ በምድርም በሰማይም ያስጠይቀናልና ላለፈው በደላችን ንስሐ ገብተን ለወደፊቱ ራሳችንን እንጠብቅ መልእክታችን ነው፡፡ በሕግ ያልተወሰንን ወጣቶችም የራሳችን አጋር እስኪትመጣልን ድረስ ፈቃደ ሥጋችንን ልንቈጣጠር ይገባል፡፡ “ከሴት ጋር የሚያመነዝር ግን አእምሮው የጐደለ ነው እንዲሁም የሚያደርግ ነፍሱን ያጠፋል፤” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ምሳ. ፮፥፴፪)፣ የዝሙት ኀጢአት ሰይጣናዊ ደዌ ነውና በዝሙት ኀጢአት የምንኖር ዂሉ የሰይጣንን አሽክላ ሰባብረን በራሳችን ጊዜ ከገባንበት እስራት ነጻ እንውጣ፡፡ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሔደንም እንፈወስ፡፡

ወደ ቀደመ ርእሳችን እንመለስና ባልና ሚስት በሕይወተ ሥጋ እያሉ ሊፋቱ የሚችሉት በአመንዝራ (በዝሙት) ምክንያት ነው፡፡ የፍትወት ፆር ከመበርታቱ የተነሣ ከትዳር አጋር አልፎ ወደ ሌላ የሚሔድ ካለ ስለ አንደኛው ደኅንነትና ስለ ጋብቻ ክቡርነት፣ እንደዚሁም ስለ ሥጋ ወደሙ ቅድስና ሲባል መፋታት ይፈቀዳል፡፡ አምላካችን “ኢትዘሙ፤ አታመንዝር” በማለት እንዳስተማረን ዝሙት መሥራት ኃጢአት ነው (ዘፀ. ፳፥፲፬)፡፡ ቢቻል ከኀጢአት ተለይቶ ለመኖርና በጽድቅ ሥራ ለመትጋት መሽቀዳደም ተገቢ ነው፤ ኾኖም ኀጢአት እየሠሩ አብሮ ከመኖር ተለያይቶ በጽድቅ መኖር ይገባልና ከመዘሞት መፋታት ይሻላልና፡፡ ደግሞም በአንድነት ወደ ገሃነመ እሳት ከመጣል ይልቅ ተለያይቶ ወደ መንግሥተ ሰማያት መግባት ይመረጣል፡፡ “… ሁለት ዓይና ኾነህ ወደ ገሃነመ እሳት ከምትገባ ይልቅ አንድ ዐይና ኾነህ ወደ መንግሥተ ሰማያት ብትገባ ይሻልሃልና” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ማቴ. ፭፥፳፱-፴)፡፡

ይህ ሲባል ግን የሐሰት ወሬ በመስማትና በይኾናል (በጥርጥር) ብቻ ለመፋታት መወሰን ተገቢ አይደለም፡፡ ከተጋቢዎቹ አንዱ ወይም ሁለቱም በዝሙት እየወደቁ ከኾነና በንስሐ መመለስ ካልቻሉ ፍቺ ይፈጸማል፡፡ በጋብቻ ወቅትም ይኹን ከጋብቻ በፊት ወይም በኋላ መዘሞት (መሴሰን) አስነዋሪ ድርጊት ነው፡፡ ስለዚህም መፋታት ከሚቻልባቸው መንገዶች አንዱ ዝሙት እንዲኾን ተደንግጓል፡፡ ይህም ዝሙት ቊርባንን ከማፍረሱም ባለፈ ከጋብቻ ውጪ ልጅ መውለድን፣ እንደዚሁም በጥንዶቹም፣ በልጆቻቸውም ላይ ሞትን ያመጣልና የሰውን ልጅ ከጥፋት ለመታደግ ነው፡፡

ከዚህ ላይ ልብ ማለት የሚገባን ቁም ነገር ቢኖር ወንድም ኾነ ሴት በዝሙት ምክንያት የተፈቱትን ማግባት አይፈቀድላቸውም፡፡ “ያለ ዝሙት ምክንያት ሚስቱን የሚፈታ ዂሉ አመንዝራ ያደርጋታል፤ የተፈታችውንም የሚያገባ ዂሉ ያመነዝራል” እንዳለ ጌታችን (ማቴ. ፭፥፴፩)፡፡ ማግባት የሚቻለው ንስሐ ግበተው፣ ከዝሙት ርቀው፣ ራሳቸውን ጠብቀው፣ በቅዱስ ሥጋው በክቡር ደሙ ተወስነው ከሚኖሩት ወገን ነው፡፡ ዂሉም ምእመናን በዚህ ክርስቲያናዊ ግብር መኖር መንፈሳዊ ግዴታችን ነውና፡፡ “ኢይደልዎ ለመኑሂ ከመ ያውስብ ብእሲተ ኅድግተ እምዝሙት በጕጕዓ አላ ይጽናሕ እስከ ትኔስሕ፤ ስትሰስን ተገኝታ የተፈታችዉን ሴት ለማንም ፈጥኖ ማግባት አይገባውም፡፡ በንስሐ እስክትመለስ ድረስ ይጠብቅ እንጂ” እንዲል ፍትሐ ነገሥት፡፡

ይቆየን

የጋብቻ ሕይወት እና የሩካቤ ሥርዓት – ክፍል ፮

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ፲፮ ቀን ፳፻፲ .

ጋብቻ በእግዚአብሔር ፈቃድ፣ በሁለት ተፈላላጊ ፆታዎች ስምምነት የሚገነባ መንፈሳዊ ተቋም ነው፡፡ “ወንህነሰ ንብል ከመ ሰብሳብ ንጹሕ ወልደት ዘአልቦ ርኵስ፤ እስመ ፈጠሮሙ እግዚአብሔር ለአዳም ወለሔዋን ከመ ይብዝኁ ሕዝብ፤ እኛስ ጋብቻ ንጹሕ እንደ ኾነ፣ ልደትም ርኵሰትም እንደሌለበት እንናገራለን፡፡ ሕዝቡ ይበዙ ዘንድ እግዚአብሔር አዳምንና ሔዋንን ፈጥሯቸዋልና” እንዳሉ ቅዱሳን ሐዋርያት (አመክንዮ)፡፡ ስለኾነም ሃይማኖትን የሚያስክድ፣ ንጽሕናን የሚያሳጣ ፈተና እንደዚሁም ሞት ካልኾነ በቀር መሠረቱ እግዚአብሔር ነውና ጋብቻ እንዲሁ አይፈርስም፡፡

ለዚህም ነው ባልና ሚስት ሥርዓተ ተክሊል በሚፈጽሙበት ዕለት በሕመም፣ በችግር ወይም በሌላ ጥቃቅን ምክንያት እንደማይለያዩ በእግዚአብሔር ፊት የመሐላ ቃላቸውን የሚሰጡት፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ከሚገጥመን ልዩ ልዩ ፈተና ሁሉ እንዲጠብቀንና መፍትሔ እንዲያመጣልን ወደ ትዳር ሕይወት ከመግባታችን በፊትም ኾነ ከገባን በኋላ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብ የሕይወት መመሪያችን ብናደርግ ሕይወታችን የተስተካከለ ይኾናል፡፡ በእግዚአብሔር ቃል የተሰበረ ልብ መንፈሳዊነትን ያላብሳልና፡፡ መንፈሳዊነት ደግሞ ፍቅርን እንጂ ጥላቻን አያስቀድምም፤ መቀራረብን እንጂ መለያየትን አይመርጥም፡፡

ጌታችን “ቃሌን ሰምቶ የሚያደርገው ዂሉ ቤቱን በዓለት ላይ የሠራ ልባም ሰውን ይመስላል፡፡ ዝናብም ወረደ፤ ጐርፍም መጣ፤ ነፋስም ነፈሰ፤ ያንም ቤት ገፋው፡፡ በዓለት ላይም ስለ ተመሠረተ አልወደቀም፤” በማለት እንደ ተናገረው (ማቴ. ፯፥፳፭)፣ ቃሉን በሕይወቱ የተገበረ ክርስቲያን ምንም ዓይነት ፈተና ቢደርስበት ሳይሰናከል ሃይማኖቱን ይጠብቃል፡፡ እንደዚሁ ዂሉ በጋብቻ የሚኖሩ ክርስቲያኖችም ልዩነታቸውን በማጥበብ በጋራ ይኖራሉ እንጂ መፋታትን አይመርጡም፡፡

በመንፈሳዊ ፍቅር የሚያምን ክርስቲያን በየሰበቡ ጥላቻን አያመነጭም፤ ትዳሩን ለማፍረስም አይጣደፍም፤ ነገሮችን በጥንቃቄ ይመረምራል እንጂ፡፡ ፍቅር፣ ትዕግሥትን፣ እዝናትን፣ መተሳሰብን፣ ትሕትናን፣ ቅንነትን፣ ጽድቅንና ተስፋን ያመጣልና፡፡ “ፍቅር ያስታግሣል፤ ያስተዛዝናል፤ ፍቅር አያቀናናም፤ ፍቅር አያስመካም፤ ፍቅር ልቡናን አያስታብይም፡፡ ፍቅር ብቻዬን ይድላኝ አያሰኝም፤ አያበሳጭም፤ ክፉ ነገርን አያሳስብም፡፡ ጽድቅን በመሥራት ደስ ያሰኛል እንጂ፣ ግፍን በመሥራት ደስ አያሰኝም፡፡ በዂሉ ያቻችላል፤ በዂሉም ያስተማምናል፡፡ በዂሉም ተስፋ ያስደርጋል፤ በዂሉም ያስታግሣል፤” ተብሎ እንደ ተጻፈ (፩ኛ ቆሮ. ፲፫፥፬-፯)፡፡

ጋብቻ ክቡር፣ መኝታውም ቅዱስ እንደ መኾኑ አንድ ባል ለአንዲት ሚስት፤ አንዲት ሚስት ለአንድ ባል ኾነው እንዲኖሩ እግዚአብሔር አምላካችን ሥርዓት ሠርቶልናል፡፡ አምላካችን “ሰው ብቻውን ይኖር ዘንድ መልካም አይደለም፤ ስለዚህ የምትረዳውን ጓደኛ እንፍጠርለት” እንጂ “የሚረዱትን ጓደኞች እንፍጠርለት” አላለም (ዘፍ. ፪፥፲፰)፡፡ ይህም አንድ ወንድ ለአንዲት ሴት፤ አንዲት ሴት ለአንድ ወንድ መፈጠሯን የሚያመለክት ነው፡፡ ይህን አምላካዊ ሕግ በመጣስ በሚስት ላይ ሌላ ሚስት፤ በባል ላይ ሌላ ባል መደረብ ነውርም ኀጢአትም ነው፡፡ ከብዙ ወንዶች (ሴቶች) ጋር መዘሞት፤ የትዳር አጋርን በየጊዜው መቀያየር የእግዚአብሔርን ሕግ መተላለፍ ነው፡፡ ከዚህም ባሻገር ቅዱሱን ጋብቻ ማሳደፍ፤ ሰውነትንም ማቈሸሽ ነው፡፡ እንደዚህ የምናደርግ ሰዎች ካለን ይህ ልማዳዊ ኀጢአት ፍጻሜው ውርደትና ሞት መኾኑን በመረዳት በንስሓ ልንመለስ ይገባናል፡፡

፩.፯ ፍቺ እና ሁለተኛ ጋብቻ

ጋብቻ፣ ዓላማውም ጠባዩም አንድነት ነው፡፡ ስለዚህም በጋብቻ ሕይወት መፋታት እንደማይገባ ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ ምክንያቱም ጋብቻ እስከ ሞት ድረስ አብረው የሚዘልቁበት፣ ዘርን የሚተኩበትና ልጆችን ወልደው ለቁም ነገር የሚበቁበት፣ በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተው ከኖሩበት ደግሞ ሰማያዊ መንግሥትን የሚወርሱበት የአንድነት ሕይወት ነውና፡፡ ስለኾነም እንዲሁ በቀላሉ አይፈርስም፤ ጥንዶቹም በሰበብ አስባቡ ሊፋቱ አልተፈቀደላቸውም፡፡

ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ባልና ሚስት ሕይወት ሲያስተምር “ፈጣሪ በመጀመሪያ ወንድና ሴት አደረጋቸው፡፡ ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል፤ ከሚስቱም ጋር ይተባበራል፡፡ ሁለቱም አንድ ሥጋ ይኾናሉ፡፡ ስለዚህ አንድ ሥጋ ናቸው እንጂ ወደ ፊት ሁለት አይደሉም። እግዚአብሔር ያጣመረውን እንግዲህ ሰው አይለየው” በማለት አንድነታቸው እንደማይለያይ ማስተማሩ መፋታት ተገቢ አለመኾኑን ያስረዳናል (ማቴ. ፲፱፥፭-፮)፡፡

በተመሳሳይ ትምህርት “እግዚአብሔር የሕይወትን መንፈስ አንድ አድርጎ ጠብቆልን የለምን? እርሱም የሚፈልገው ምንድር ነው? ዘር አይደለምን? ስለዚህ መንፈሳችሁን ጠብቁ፤ ማንም የልጅነት ሚስቱን አያታልል፡፡ ‹መፋታትን እጠላለሁ› ይላል የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር፤” በማለት ባልና ሚስት ሊፋቱ እንደማይገባ ነቢዩ ሚልክያስ ተናግሯል (ሚል. ፪፥፲፭)፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም “ሚስትም ከባልዋ አትለያይ፤ ብትለያይ ግን ሳታገባ ትኑር፡፡ ወይም ከባልዋ ትታረቅ፤ ባልም ሚስቱን አይተዋት … በሚስት ታስረህ እንደ ኾንህ መፋታትን አትሻ” በማለት ፍቺ ተገቢ አለመኾኑን አስተምሯል (፩ኛ ቆሮ. ፯፥፲-፳፯)፡፡

መምህራነ ቤተ ክርስቲያንም የቅዱሳት መጻሕፍትን ቃለ ትምህርት መነሻ አድርገው “ወአልቦ ዘይጸልዕ እግዚአብሔር ዘየዐቢ ኃጢአት ዘእንበለ ዘይድኅር ብእሲቶ ወያወስብ ካልእተ …፤ ሚስቱን ፈትቶ ሌላ ከሚያገባ ሰው የበለጠ እግዚአብሔር የሚጠላው ኀጢአት የለም፡፡ ይህ ሥራ በእግዚአብሔር ዘንድ የተናቀ ነውና፡፡ በነቢያትና በሐዋርያት ሥልጣንም የተለየ (የተወገዘ) ነውና” ሲሉ የባልና ሚስት መፋታት በእግዚአብሔር ዘንድ የተጠላ ተግባር መኾኑን ይናገራሉ (ተአምረ ማርያም፣ ፲፩ኛ ተአምር፣ ቍ. ፳፰)፡፡

የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ በፍቅርና በአንድነት መኖርን የሚሰብክ በመኾኑ ፍቺን አጥብቆ ይከለክላል፡፡ ከተጋቡ በኋላ የሕይወት መሰናክሎችን በመፍታት አብሮ መኖር እንጂ መለያየት ክርስቲያናዊ ሥርዓት አይደለምና፡፡ በመኾኑም ችግሮችን በውይይት በመፍታት፣ በመመካከርና በመፈቃቀር ተስማምቶ እስከ ሞት ድረስ መኖር ተገቢ ነው፡፡ ነገር ግን በትዳር ሕይወት እጅግ የከበደና መፍትሔ የሌለው ችግር ሊመጣ ይችላል፡፡ በዚህ ጊዜ ለጉዳዩ መፍትሔ በሚያመጣ መልኩ መወያየት፣ ከንስሓ አባት ጋር መመካከር፣ በጾም በጸሎት መትጋትና እግዚአብሔርን መማጸን ይገባል፡፡

ኾኖም በመካከላቸው በሃይማኖት ወይም ሊፈታ በማይችል ልዩ ልዩ ምክንያት ለጉዳትና ለሞት የሚያደርስ ግጭት በተደጋጋሚ ከተከሠተ፤ አንዳቸው ወይም ሁለቱም ከትዳር ውጪ ከሔዱ (ዝሙት ከፈጸሙ) እነዚህን ችግርች በምክክር መፍታት፣ በንስሓም ማጽዳት ካልተቻለ መፋታት ይፈቀዳል፡፡ ከዂሉም በላይ ከሁለቱ አንዱ በሞት ከተለየና በሕይወት የቀረው አካል ጋብቻ መመሥረት ከፈለገ ሁለተኛ ማግባት ይቻላል፡፡ ያም ኾኖ ግን በሕገ ቤተ ክርስቲያን ከተጠቀሰው ምክንያት በቀር መፋታት አይገባም (ፍትሐ ነገ. አን. ፳፬፣ ቍ. ፲፩-፲፯)፡፡

ከላይ በተጠቀሱ ምክንያቶች መፋታትና ሁለተኛ ጋብቻን መመሥረት ቢቻልም ከዚያ በፊት ችግሮችን በውይይት ለማስተካከልና ለመስማማት ከፍተኛ ጥረት ማድረግ እንደሚገባን መዘንጋት የለብንም፡፡ ምክንያቱም ‹‹መፋታት ይፈቀዳል›› በሚል ሰበብ በሚረባውም በማይረባውም ጉዳይ ጋብቻን ማፍረስ ተገቢ አይደለምና፡፡ ነገር ግን እጅግ የከበደና መፍትሔ የሌለው ችግር ከመጣ ቀደም ሲል እንደ ገለጽነው መፋታትና አስፈላጊ ከኾነም ሁለተኛ ጋብቻ መመሥረት ይፈቀዳል፡፡ በዚህ መልኩ የተፋቱ ጥንዶች አስፈላጊነቱ ተጣርቶ እስከ ሦስት ጊዜ ድረስ ጋብቻ ሊፈጽሙ እንደሚችሉ በሕገ ቤተ ክርስቲያን ተወስኗል፡፡ ከሦስት ጊዜ በላይ ጋብቻን መፈጸም ግን እንደ ዝሙትና እንደ ርኵሰት ይቈጠራል፡፡

“እስመ አውስቦ ቀዳማዊ ዘበአሐቲ ብእሲት፤ ወአውስቦሰ ዳግሚት ካልእት ተሐፅፅ እምቀዳሚት፡፡ ወአውስቦሰ ሣልስ ምኑን ውእቱ፤ ወአልቦ በኀቤነ እምድኅረዝ አውስቦ ሕጋዊ፤ በአንዲት ሴት የሚኾን (የሚፈጸም) የመጀመሪያ ጋብቻ ደግ ነው፤ ሁለተኛይቱ ግቢ ከመጀመሪያይቱ ታንሳለች፡፡ ሦስተኛው ግቢ ግን የተናቀ ነው፡፡ ከሦስተኛው ግቢ በኋላም መጽሐፍ ያዘዘው ግቢ የለም፤” እንዲል (ፍት. ነገ. አን. ፳፬፣ ክፍ. ፩፣ ቍ. ፵፮-፵፫)፡፡ ጉዳዮቹን በመጠኑ ለመዳሰስ ያህል፣ ሁለተኛ ጋብቻ (ፍቺ) ከሚፈቀድባቸው መንገዶች መካከል ዋና ዋናዎቹን እንደሚከተለው አቅርበናቸዋል፤

ይቆየን