ሁሉን መርምሩ መልካሙን ያዙ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአምልኮተ እግዚአብሔር ከሦስት ሺሕ ዘመን ላላነሰ የቆየውን የኢትዮጵያውያንን የሃይማኖት ሕይወት ስትመራና አሁንም በመምራት ላይ ያለች ከመሆኑ አንጻር ዘርፈ ብዙ የጥናትና ምርምር ሥራ እንዲደረግባት የምትጋብዝ ናት፡፡
ቤተክርስቲያናችን በታሪኳ ከፍተኛ የሥነ-ሕንፃና ሥነ-ጽሑፍ፣ የፍልስፍና፣ የሕግና የአስተዳደር፣ የዘመን አቆጣጠር፣ ከፍተኛ የማኅበራዊ ግንኙነትና የባህል መሠረት ናት፡፡

ቤተክርስቲያናችን በቅዱሳት መጻሕፍት ትምህርትና ቀኖና፣ በትምህርተ ሃይማኖት፣ በሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን፣ በትውፊትና ታሪክ በኩልም ለጥናትና ምርምር የሚጋብዝ ከፍተኛ ክምችት አላት፡፡ የዚህ ክምችት ኃይልም ቤተክርስቲያኒቱን የሀገሪቱ የጥናትና ምርምር ዒላማ አድርጓታል፡፡ በሀገራችን ያሉ የኢትዮጵያ ጥናት ላይ የሚያተኩሩ ተቋማት የምርምር ትኩረት በአብዛኛው በቤተ ክርስቲያናችንና ባሏት ዘርፈ ብዙ ቅርሶች ላይ እንዲሆንም አስገድዷል፡፡

በተለይም ሀገራችንና ቤተክርስቲያናችን በታሪክ ዘመን ውስጥ ብዙ ወርቃማ ዘመናትን ቢያሳልፉም፤ በዮዲት፣ በግራኝ፣ በዘመነ መሳፍንት፣ በጣሊያንና በእርስ በእርስ ጦርነቶች የተፈጠረው ምስቅልቅል በቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊና ቁሳዊ ሀብት ቅብብሎሽ ላይ የፈጠረው ክፍተት ለበርካታ ሊቃውንት የጥናት ጉዳዮች ምንጭ ነው፡፡ በሃይማኖት ትምህርት በኩልም የአይሁድ፣ የካቶሊካውያን፣ የቅባትና የጸጋ ሌሎች የሥጋ ፍልስፍናዎችና የሟርትና ጥንቆላ ሥራዎች በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ዙሪያና ውስጥ ሆነው እውነተኛውን አስተምህሮ ሲፈታተኑት በመኖራቸው እነርሱን በመከላከል በኩል የተደረጉ ተጋድሎዎችና ያረፉ ተጽዕኖዎች ለጥናት የሚጋብዙ አንኳር ጉዳዮች ናቸው፡፡

ይሁን እንጂ የጥናትና ምርምር ሥራን ዘመናዊ ከማድረግና የራሳችንን ታሪክ ባህልና አጠቃላይ ገጽታ ከማጥናት አንጻር ሚና የነበራቸው ኢትዮጵያውያን ያልሆኑ፣ በሃይማኖትም ኦርቶዶክሳውያን ያልሆኑ ወገኖች ነበሩ፡፡ አንዳንዶቹ ተመራማሪዎች በጥናቶቻቸው በሚሰጧቸው ድምዳሜዎች ኢትዮጵያውያን ጥያቄ እንዲያነሡባቸው፤ በጥርጣሬም እንዲታዩ አድርጓል፡፡ ከኢትዮጵያውያን ውጪ የሚደረጉ ጥናቶች ላይ ሁሉ ጥርጣሬ ማሳረፍ አግባብ ባይሆንም የኢትዮጵያውያን የጥናት ተሳትፎ በሚፈለገው ልክ ባለመሆኑ የጥናትና ምርምር ሥራዎች በኢትዮጵያ ሊቃውንት ትኩረት ማግኘት እንዳለባቸው ግን ሁሉንም ያግባባል፡፡
 
መጽሐፍ ሁሉን መርምሩ መልካሙን ያዙ እንዳለ በሊቃውንቱ መካከል በአንዳንድ ጉዳዮች ላይ የገለጻ ወይም የሐሳብ ልዩነት ሲፈጠር ያለ ግጭት ለመፍታት አንድነትንም ለማጽናት በጥናትና ምርምር ሥነ-ምግ ባር ላይ ተመሥርተው የሚዘጋጁ ጥናትና ምርምሮች ፍቱን መድኃኒቶች ናቸው፡፡ በተለይ በዚህ ዘመን በራሳቸው ፈቃድና በቅጥረኝነት ተነሣሥተው የቤተክርስቲያናችንን አዋልድ መጻሕፍት፣ ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን፣ ታሪክና ትውፊት ለሚያብጠለጥሉ ከዚያም በግርግር ቤተክርስቲያንን አንድነቷን ለማናጋት ለሚጥሩ የተሐድሶ መናፍቃን ልጓም ያበጃል፡፡ ጠንካራ የጥናትና ምርምር ተቋማት ለቤተ ክርስቲያናችን የሊቃውንት ጉባኤም ለቅዱስ ሲኖዶስ አገልግሎት ግብዓት ከማቅረብ አንጻርም ትልቅ ሚና ይኖራቸዋል፡፡ በመሆኑም ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን፣ ዘመናዊ ትምህርትንም የተከታተሉ ክርስቲያን ምሁራን ላይ የተመሠረቱ የምርምር ተቋማት መመሥረት እንዳለባቸው ማኅበራችን የጸና እምነት አለው፡፡ ለዚህም የሚመለከታቸው አካላት ጥናትና ምርምር ጊዜው የሚጠይቀውና የቤተ ክርስቲ ያናችንን አንድነት በሀገራችንም ውስጥ ያላትን ግንባር ቀደም ሚና መጫወት እንድትችል አዎንታዊ ሚና እንዳለው ተገንዝበው አስፈላጊውን ሁሉ ሊፈጽሙ ይገባል እንላለን፡፡

የቤተክርስቲያን አስተዳደርም የጥናትና ምርምር ተቋማትን መሥርተው ለመንቀሳቀስ ለሚፈልጉ የክር ስቲያን ወገኖች ምቹ ሁኔታ መፍጠርና እነርሱን የሚያስተናግድ አሠራርና መዋቅራዊ ሁኔታ ማመቻቸት ይገባዋል፡፡ ጠቅላይ ቤተ ክህነትና አህጉረ ስብከቶች ጥናቶች እየተዘጋጁ የሚቀርቡባቸው ጉባኤዎችን በተወሰኑ ጊዜዎች ሊያዘጋጁ ይገባል፡፡ ጥናትና ምርምር የራሱን የአስተዳደሩን የመፈጸም አቅም የበለጠ የሚያጠናክር በመሆኑ ተግባሩን መደግፍ ብልህነት ነው፡፡ በጥንቃቄና በብዙ ሊቃውንት የተዘጋጁ የጥናት ውጤቶችም ጥቅም ላይ እንዲውሉ መጣር አለበት፡፡ ጥናትና ምርምር ተቋምን መመሥረት ከፍተኛ ጥረት የሚጠይቅ መሆኑ የሚታወቅ ሲሆን ቢያንስ ለጥናትና ምርምር ተግባር የሚያግዙ ቤተ መጻሕፍት፣ ቤተ መዛግብትና ሙዚየሞችን በየደረጃው ማደራጀትና ማስፋፋት ለነገ የሚባል ተግባር አይደለም፡፡

ሊቃውንተ ቤተክርስቲያንና ሌሎች ክርስቲያን ምሁራን ይህንን ተግባር ለመደገፍ ያሉበት የዕውቀት ደረጃና ሙያ ግድ ይላቸዋል፡፡ ሊቃውንት ያለጥናትና ምርምር ተቋም ዕውቀታቸውን ማዳበር፣ ዕውቀታቸውን ማካፈል አዳዲስ መረጃዎችንም መስጠት አይችሉም፡፡ በመሆኑም ጥናትና ምርምር ተቋማት እንዲስፋፉ ግፊት ከማድረግ ጀምሮ የሚመሠረቱበትን ብልሀት፣ ከተመሠረቱም በኋላ የሚጠናከሩበትን በዘላቂነት የሚሠሩበትን መላ በመዘየድ፣ በጥናትና ምርምር ሥራዎች በመሳተፍ የጥናትና ምርምር ሥራዎችንም በማስተዋወቅ ሰፊ አስተዋጽኦ ሊያደርጉ ይገባል እንላለን፡፡

በአጠቃላይ ሕዝበ ክርስቲያኑ የጥናትና ምርምር ተቋማትን ከመመሥረት ጀምሮ እስከ ማጠናከር ድረስ በሚደረገው ርብርብ በገንዘባቸው፣ በጉልበታቸው፣ በዕውቀታቸውና አስፈላጊውን አስተዋጽኦ ማድረግ ይገ ባቸዋል፡፡ ቤተክርስቲያናችን ካላት ክብር፣ ታሪክና ቅርስ አንጻር አንድ እንኳን ጠንካራ የምርምር ተቋም ማጣቷ ቆጭቶን አስፈላጊውን ሁሉ ልንፈጽም ይገባል፡፡ ቤተክርስቲያናችን አሉባት የምንላቸውን ችግሮች ሁሉ ለመፍታት ጥናትና ምርምር ያለውን ወሳኝ ሚና በመረዳት የክርስቲያን ወገን ሁሉ ሊረባረብ ይገባዋል፡፡ ቅርሶቻችን እየጠፉ፣ መጻሕፍቱ እየተበረዙ፣ እየተመዘበሩ፣ በአስተዳደራዊ ችግሮች እየታመስን ባለንበት ወቅት፤ የኢኮኖሚ፣ የማኅበራዊ የአካባቢ ጥበቃ ጉዳዮች የቤተ ክርስቲያን አስትዋጽኦ ተፈላጊ በሆነበት በዚህ ጊዜ የጠራና የነጠረ ሐሳብ ይዘን መራመድ ካልቻልን የሚያ ጋጥመን ፈተና ቀላል አይሆንም፡፡ ሰንበት ትምህርት ቤቶችና ማኅበራትም ባሉበት ደረጃ ከቤተ መጻሕፍት ጀምሮ እስከ ከፍተኛ የምርምር ተቋም ድረስ በቤተ ክርስቲያናችን የማስፋፋት ርእይ ሊኖራቸው ይገባል፡፡

ማኅበራችን ማኅበረ ቅዱሳንም ይህንን ወሳኝ ተግባር ከመፈጸም አንጻር አርአያ ለመሆን ጥረት እያ ደረገ ይገኛል፡፡ ለሚያደርገው ጥረትም ማሳያ የሚሆን የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ጥናት መጽሔት /Journal/ በቅርቡ ማውጣቱ የዚህን ተግባር ወሳኝነት ለማጉላት ነው፡፡ በመሆኑም ሁሉም የሚመለከታቸው ወገኖች በየደረጃው የጥናትና ምርምር ተቋማትን ለጥናትና ምርምር መመሥረት አስተዋጸኦ የሚያደርጉ ሌሎች የመረጃ ማእከላትን ማቋቋም ይገባቸዋል እንላለን፡፡

mk20thyearCD

ኢንኅድግ ማኅበረነ

mk20thyearCD

በ«ተሐድሶ» መሰሪ እንቅስቃሴ ላይ ዛሬም እንንቃ!

ኢትዮጵያ  ያላት ክብርና ታሪክ በመጽሐፍ ቅዱስ በተለያዩ የታሪክ ሰነዶች የተመሰከረ፣ በታላላቅ ማራኪ ቅርሶችም የታጀበ ነው። የነበራት ክብርና ገናናነት ከምዕራብ እስከ ምስራቅ፣ ከሰሜንም እስከ ደቡብ  የታወቀ ነው። ከዚህ ጉልህ ታሪክ ውስጥ የበለጠ ጎልቶ የሚታየው ደግሞ የሀገራችን የሃይማኖት ታሪክ ነው። ኢትዮጵያ ከእስራኤል ወገን ቀጥሎ ብሉይ ኪዳንን በመቀበል ቀዳሚ ሀገር ናት። በመሆኑም በዘመነ ብሉይ ሕግና ነቢያትን በመቀበልና በመፈጸም እንዲሁም የተስፋውን ቃል በመጠበቅ ኖራለች። ጊዜው ሲደርስም የሐዋርያትን ስብከት ተቀብላ የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነትና ጌትነት አምና ጥምቀትን ወደ ምድሯ አምጥታለች። በመሆኑም ወንጌልን ተቀብላ አምና ስትሰብክ ኖራለች። አሕዛብ ሕግና ነብያትን በናቁበት ጊዜ ከአሕዛብ ወገን ቀድማ ከእስራኤል ሕዝብ ጋር ኦሪትን በመቀበሏ እንዲሁም ደግሞ እስራኤል ወንጌልን በናቁበት፣ ክርስቶስን በጠሉበት ጊዜ ከአሕዛብ ጋር ሐዲስ ኪዳንን በጊዜው በመቀበሏ ሁለቱንም ኪዳናት በጊዜያቸው ያስተናገደች ብቸኛ ሀገር ናት ማለት ይቻላል። ስለዚህ በዓለምም ሆነ በአፍሪካ መድረክ የሚያስከብር የሃይማኖት ታሪክ ባለቤት ናት። ከዚያም በመነጨ ሊሻሩ ከማይችሉት ከሕግና ከነቢያት እንዲሁም ከክርስቶስ ወንጌል፣ ከሐዋርያት ትምህርት፣ ከሊቃውንቱም ትርጓሜ የመነጨ ሰውንም እግዚአብሔርንም ደስ የሚያሰኝ ሥርዓተ አምልኮ ባለቤት ለመሆን አስችሏታል።
 
ይህ ብዙዎችን የሚያስደስተውን ያህል አንዳንዶች ደግሞ በቅናት የሚመለከቱትና ለራሳቸው ፍላጎት ማሰፈጸሚያ አበላሽተው ሊጠቀሙበት ሲቋምጡ ታይተዋል፤ እየታዩም ነው። ይህንንም ታሪክ ለማጥፋት ወይም ባለበት በርዞ ከልሶ የራሳቸውን ኑፋቄና የክህደት አጀንዳ ለማስፈጸም ይሻሉ። በተለይ የምዕራቡ ዓለም «የካህኑ ንጉሥ» ሀገር እያለ የሚጠራትን ኢትዮጵያን ከመስቀል ጦርነት ጀምሮ በመካከለኛው ምስራቅና በአፍሪካ ለሚከተሉት ለየትኞቹም አጀንዳዎቻቸው መንደርደሪያ የማድረግ ጽኑ ፍላጎት እንዳላቸው ግልጽ ነው። ይህ እውን እንዲሆን ደግሞ ለሀገሪቱ አንድነት፣ ሉዓላዊነት፣ ለባህላዊና ማኅበራዊ ትስስር መሠረት ነች የሚሏትን የኦርቶዶክስ ቤተክስቲያን መቆጣጠር፤ በእነርሱም ርዕዮት ማራመድ፤ ካልሆነም ማዳከም፤ ከተቻለም መከፋፈል ይፈልጋሉ።
 

ይህንንም ከሱስንዮስ ዘመን ጀምሮ ለማድረግ የሚችሉትን ያህል ጥረዋል። ይህንን መሰል ቅሰጣና ሰርጎ ገብነት በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን የሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን በመሰሉ ሌሎችም አብያተ ክርስቲያናት ላይ ለመፈጸም ተንቀሳቅሰዋል። ለዚህም በሕንድ ቅኝ ገዢ የነበሩት ፖርቹጋሎችና እንግሊዞች ዋነኞቹ ተጠቃሾች ናቸው። በሚገርም ሁኔታ ኢትዮጵያም ውስጥ ተቀራራቢ በሆነ ጊዜ እነዚሁ ኃይሎች የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን ለማዳከም ለማጥፋት ተንቀሳቅሰዋል። ለዚህም በሱስኒዮስ መንግሥት ጊዜያዊ ድጋፍ አግኝተው በነበሩት በነፔድሮኤዝ የሚመራው የፖርቹጋል ሚሲዮናውያን ጥማታቸውን ለማርካት ቢተጉም በኢትዮጵያውያን ሊቃውንትና ምእመናን ጥረት ከሽፏል።
 

ሕንድ ውስጥ ይንቀሳቀስ የነበረው ቸርች ሚሽነሪ ሶሳይቲ /CMS/ የተባለው የአንግሊካን ፕሮቴስታንቶች ሚሽን በንጉሥ ሳህለ ሥላሴ ዘመን አይዘንበርግና ክራፕፍ የተባሉ ግለሰቦችን ወደ ኢትዮጵያ ከመላክ ጀምሮ በተከታታይ በሌሎችም ሚሽነሪዎች ጥረት ቢያደርግም ከስለላ ያለፈ ፋይዳ አልነበረውም። ቅኝ አገዛዙም ሆነ ቤተክርስቲያኒቱን ካቶሊካዊ  ወይም ፕሮቴስታንት የማድረግ ወይም የመከፋፈሉ ሁኔታ ሕንድ ውስጥ እን ደያዘላቸው በዚህ ሀገር ሊሳካ አልቻለም፤ ሌላ በኦርቶዶክሳዊነት ስም የተመሠረተ የተለየ የእምነት ተቋም የለምና።
 

በቤተክርስቲያኒቱ በእነርሱ ምክንያት ወይም በሌላ ምክንያት የሚፈጠሩ ልዩነቶችን በነገሥታቱና በሊቃውንቱ ከፍተኛ ጥረት በጉባኤዎች እየተፈቱ ያለምንም የውጭ ኃይሎች ጣልቃ ገብነት አንድነታችንን ጠብቀን ኖረናል። ይህም ለቤተክርስቲያን ብቻ ሳይሆን ለሀገር አንድነትም መሠረት ሆኗል።

የሀገሪቱ ነጻነትና አንድነት እንዲሁም ለረጅም ዘመን የኖረ የሃይማኖት ታሪክ ባለቤትነት በተለይ አፍሪካውያንንና የዓለምን ጥቁር ሕዝቦች እየሳበ መምጣቱ ለእነዚህ ኃይሎች የበለጠ የሚያንገበግብ ሆኖባቸዋል። ስለዚህ መላውን አፍሪካና ሌላውንም ሕዝብ ለመማረክ የኢትዮጵያን ቤተክርስቲያን መቆጣጠር፤ የተለየና የተወገዘ አስተምህሮአቸውን መጫን ወይም አንሸራቶ ማስገባት፤ ካልሆነም አዳክሞና አጥፍቶ ሌላ መሠረት በመሥራት ወደሌላው ወገን  የመዝመት ብርቱ ዓላማ አላቸው።

 

በተለይ በአሁን ጊዜ ማንኛውም ወገን በሀገሪቱ የራሱን ሃይማኖት በነጻነት የማራመድ መብት ያለው በመሆኑ የራሳቸውን አምልኮ የሚፈጽሙበት በዓይነት ብዙ ድርጅት ቢኖራቸውም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በዓለም ላይ ያላትን የሃይማኖት ታሪክ ክብርና ትኩረት ያህል የማግኘት ምንም እድል እንደሌላቸው ተገንዝበዋል። በመሆኑም ሌላ ዘርፈ ብዙ መላ መዘየድ ጊዜው ጠይቁአቸዋል። ለዚህ የመረጡት አካሔድ «ተሐድሶ» የተባለውን የመናፍቃን ተላላኪ ኃይል በቤተክርስቲያን ውስጥ ማስረግ ነው።

 

«ተሐድሶ» የተባለው በተለያዩ መናፍቃን የሚደገፍ፣ ተቋማዊ ሆኖ ያልተደራጀ፣ ወጥ አስተምህሮ የሌለው፤ ነገር ግን ኦርቶዶክሳዊ ነኝ ብሎ የተሰለፈ፤ በየትኛውም መንገድ የቀጠሩትን የተለያዩ የመናፍቃን ፍላጎት ለማርካት  ቤተክርስቲያንን ለመቆጣጠር በውስጥና በውጭ ያሸመቀ ኃይል ነው።  ከዚህ ቀደም ማኅበራችን ይህንኑ በኅቡዕ የተደራጀ የተወሰኑ መነኮሳት፣ መርጌቶችና  የዲያቆናት የተላላኪነትና የምንፍቅና አካሔድን ካጋለጠ ጀምሮ ግን ካህናትና ምእመናን ጉዳዩን ወደ ማጤን እንዲገቡ አስገድዷል። ይሁን እንጅ በጊዜው ለአንዳንዶች እነዚህ አካላት የቤተክርስቲያን ጠላቶች ሳይሆኑ የማኅበረ ቅዱሳን የአገልግሎት ተገዳዳሪዎች ተደርገው ይታሰቡ ነበር። ይህን ድብቅ እንቅስቃሴያቸውን የሚከታተል ታዛቢ፣ ተመልካች በየሰንበት ትምህርት ቤቱ መኖሩን፤ ካህናቱም እያንዳንዱን እንቅስቃሴ መፈተሽ በመጀመራቸው ለስውር  እንቅስቃሴአቸው በር እየተዘጋ መምጣቱን ተረዱ። በመሆኑም ያላቸው ብቸኛ አማራጭ ግእዝ ተናጋሪ መናፍቅ ሆነው፡ የቤተክርስቲያንን መዓርጋት በስማቸው እየቀጸሉ፡ ለመጻሕፍት፣ መጽሔትና ጋዜጦቻቸው ኦርቶዶክሳዊ ገጽታ እያላበሱ በግልጽ ፕሮቴስታንታዊ አስተምህሮን መዝራት ጀመሩ። ይህ ደግሞ የ«ተሐድሶ»ን እንቅስቃሴ እውነተኛ ምንነትና በቤተክርስቲያን ጠላትነት የተሰለፈ ኃይል እንጂ የማኅበረ ቅዱሳን የአገልግሎት ተገዳዳሪ አለመሆኑን በራሱ እንቅስቃሴ ግልጽ አደረገ።

 

በመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች ላይ የተመሠረተው ኑፋቄን የመዝራት ስልት በመምህራንና በሊቃውንቱ በተደረገው ለእምነት ጠበቃ የመሆን ተከታታይ እንቅስቃሴ ዋጋ እያጣ ሲመጣ ክርክራቸውን ወደ ገድላትና ድርሳናት በማዞር የነርሱን የኑፋቄ ዘር ከማምከኑ እንቅስቃሴ ሊቃውንቱ ዞር ብለው ቤተክርስቲያኒቱ ብቻ በምትጠቀምባቸው በራሷ መጻሕፍት ላይ በመከራከር ሊቃውንቱ ጊዜ እንዲያጠፉ፤ ከተቻለም በቤተክርስቲያን መከፋፈል እንዲፈጠር ተንቀሳቅሰዋል። ይህንን ለማድረግም ግእዝ ጠቃሽ ነን የሚሉ፤ በማኩረፍ፣ ጥቅምን በመፈለግና በመታለል ወዘተ ወጥተው በየጥጋጥጉ የሚወራጩ መርጌቶችን በመጠቀም ነው። ይህ ደግሞ ከመቶ ዓመት በፊት ከሁለት ምዕተ ዓመታት ላላነሰ ጊዜ የቤተክርስቲያኒቱን ሊቃውንት ሲያተራምሱበት እንደቆዩት የቅባትና የጸጋ አስተምህሮ የቤት ሥራ ዓይነት ለሊቃውንቱ የመስጠት ስልት ነው። እነዚሁ «ተሐድሶ» ብለው ራሳቸውን የሚጠሩት የመናፍቃን ተላላኪዎች ቤተክርስቲያናችንን ለመቆጣጠር ያስችለናል የሚሉትን የትኛውንም ስልት ከመጠቀም ወደኋላ የማይሉ አካላት ናቸው። ጎሳና ጎጥን ለማናከስ፣ በፖለቲካ ጉዳዮች በማስመሰል ለመክሰስ፣ ስም በማጥፋት አንዱን በአንዱ ላይ ለማነሣሣት ወዘተ ይጥራሉ፤ እየጣሩም ነው።

የ«ተሐድሶ» ኃይል ከውጭ ተበታትኖ ያለ ፈታኝ ይምሰል እንጂ በሁለት መልኩ ተሰልፎ የሚሠራ እርስ በእርሱ የሚተዋወቅም የማይተዋወቅም ኃይል ያለው ነው። በአንድ ገጽ ከውጭ ኦሮቶዶክሳዊ ነኝ እያለ በግእዝ እየጠቀሰ፣ አሉባልታ እያራባ፣ የሊቃውንቱን ትምህርት እያጣመመ፤ ስልት በመሰለው መንገድ ሁሉ ከአርዮሳውያን ጀምሮ እስከ ንስጥሮሳውያን፣ ከሊዮን እስከ ሉተር የተነሡ መናፍቃንን ትምህርት በተለያዩ መንገዶች /መጻሕፍት በመጻፍ፣ መጽሔትና ጋዜጣ በማሳተም፣ በራሪ ወረቀት በማሳተም/ እየዘራ፡ ከቤተክርስቲያን ውጡ እያለ ወደ ውጭ የሚስብ በፈሪሳውያን መንገድ የቆመ ጎታች ኃይል /pulling power/ ነው። ሌላው ደግሞ ከውስጥ ሆኖ  አውቀውም ሆነ ሳያውቁ ለዓላማው ተባባሪ ከሆኑ የቤተክርስቲያኒቱ የውስጥ አካላት ጋር በተለያየ መንገድ ምእመናንን እያስደነበረ የሚያስወጣ ገፊ ሃይል /pushing power/ ሆኖ በአስቆርቱ ይሁዳ መንገድ የቆመ ነው።

 

በዚሀ ይሁዳዊ ግብር ውስጥ የሚሳተፈው ተላላኪ ቤተክርስቲያንን አሳልፎ ለመስጠት በሚያስችለው መመሳሰል ውስጥ ያለ ሲሆን በምእመናንና በሊቃውንቱ ፊት ተጨባጭ መረጃና ማስረጃ እስከሚቀርብብኝ ድረስ ተሰውሬ እሠራለሁ ብሎ የሚያስብ በተናጠልና በቡድን የሚሹለከለክ ኃይል ነው።

ይሄ ወገን በቤተክርስቲያናችን ውስጥ ሆኖ በተለያዩ የቤተክርስቲያኒቱ መዋቅሮች ውስጥ እንቅፋት እየፈጠረ ቤተ ክርስቲያኒቱ ብቁ አገልግሎት እንዳትሰጥ ያዳክማል። የቤተክርስቲያኒቱ አስተዳደር የበቃና የነቃ አገልግሎት ፈጽሞ ካህናትና ምእመናንን እንዳያረካ፤ በምእመናንና በሊቃውንቱ በቤተ ክርስቲያኒቱም አስተዳደር መካከል መለያየትና መጠራጠር እንዲነግሥ የበኩሉን ሚና ይጫወታል። የካህናትን ስምና ክብር በማጉደፍ ምእመናን ለክህነት ክብር እንዳይኖራቸው፤ የንስሐ አባትና ልጅ ግነኙነታቸው እንዲላላ ያደርጋል።  በካህናት ወይም በሊቃውንት አባቶች በኩል የሚታዩ ግድፈቶች ወይም ጥፋቶችን በማጯጯኽ አጠቃላይ የቤተክርስቲያኒቱ ድክመት አድርጎ በማወራረድ የሚያታልል፤ ምእመናን በቤተ ክርስቲያኒቱ አካሔድ ተስፋ እንዲቆርጡ በጋዜጣና በመሳሰሉት ብዙኃን መገናኛዎች በመዝራት ትርፍ ለማግኘት የሚጥር ነው። ብርቱ አገልግሎት በመፈጸም የቤተክርስቲያኒቱን ተልእኮ ለመወጣት ጥረት የሚያደርጉ ማኅበራትን፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን፣ መምህራንን፣ አባቶችን ስም በማጥፋት ከምእመናን ለመለይት ይንቀሳቀሳል። «ተሐድሶ» ለዚህ ግብሩ ከምእመናን ጀምሮ እስከ ታላላቅ አባቶች  ድረስ አውቀውም ሳያውቁም የአጀንዳው አስፈጻሚ ወይም መሰላል የሚሆኑ ድጋፍ ሰጭዎችን ለመመልምል ጥረት ያደርጋል:: እነዚህም አካላት የቤተክርስቲያኒቱን አሠራር እንዲያውኩ ብቻ ሳይሆን ገጽታዋን በማበላሸት መንጋው ደንብሮ እንዲበተን መሣሪያ ለማድረግ ነው:: የቤተክርስቲያኒቱን አገልጋዮች መለያ ለብሰው ወይም መስለው፣ በማይገባ ጊዜና ቦታ የማይገባ ነገር ሲያደርጉ በመታየት ምእመናንን በማስቆጣት ላይ ያሉ ሐሳዌ መነኮሳት፣ ቀሳውስት፣ ባህታውያን ወዘተ የዚህ ስልት አስፈጻሚዎች ናቸው:: በመልካም ግብር ለመጽናት ባለመቻላቸው ተስፋ ቆርጠው አላግባብ በእንዝህላልነት የሚራመዱ አንዳንድ አገልጋዮችም የዚህ የጥፋት ዓላማ ተባባሪዎች እየሆኑ ነው:: ተግባራቸው ምእመናንን ከቤተክርስቲያን አስወጥቶ  የሚጥል በመሆኑ በውስጥ እየሠራ ያለው የ«ተሐድሶ» ገፊ ኃይል መሣሪያ ሆነዋል:: ቢያንስ ምእመናንን ላለማሰናከል ጥንቃቄ ሲያደርጉ አታይምና::

ከሁሉም በላይ አሳሳቢው አካሔድ ግን የቤተክርስቲያኒቱን ሐዋርያዊ ተልእኮ ወዴትም እንዳይራመድ አሳስሮ ለማስቀመጥ፤ ይህንን የ«ተሐድሶ» መረብ በጥሰው በማለፍ ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት  የሚንቀሳቀሱ አካላትንም ከአስተዳደሩ በማ ጋጨት ወይም ለመከፋፈል በመሞከር ወዘተ ምንም ዓይነት ውጤታማ የአገልግሎት እንቅስቃሴ እንዳይደረግ የሚችለውን ያህል ጥረት ማድረግ ነው:: ቤተ ክርስቲያን ያላትን ሀብት በአግባቡ ጥቅም ላይ አውላ መንፈሳዊ አገልግሎቱን ማቀላጠፍ እንዳትችል ለማድረግ፡ ከዚያም አልፎ የካህናቱን የኑሮ ሁኔታ ሊያሻሽሉ የሚችሉ ውጤታማ ፕሮጄክቶች ስልታዊ በሆነ መንገድ ተግባራዊ እንዳይደረጉ፤ የቤተክርስቲያን የአገልግሎት ተቋማት የመፈጸም አቅም እንዳይጎለብት የተለያዩ መሰናክሎችንና ውዥንብሮችን ለመፍጠር ይጥራል:: ይህን ውዥንብር «ተሐድሶ» የሚፈልግበት ወሳኝ ምክንያት በቤተክርስቲያኒቱ አጠቃላይ አካሔድ አለመርካት እንዲኖር፤ ተስፋ መቁረጥም በምእመናንና ካህናቱ ዘንድ እንዲሰፍን፤ ከዚያም መከፋፈል እንዲፈጠር ለማድረግ ነው::በቤተክርስቲያን አካባቢ አልፎ አልፎ የሚፈጠሩ ውዝንብሮችና ዓላማና ግባቸው የማይታወቁ መጠላለፎች በቤተክርስቲያኒቱ ውስጥ ገፊ ኃይሎች ሆነው በስውርና በግልጽ የሚንቀሳቀሱ የ«ተሐድሶ» መረብ አባላትና ተባባሪዎቻቸው የሚፈጥሯቸው ውዝግቦች ናቸው::

እነዚህ ገጽታን በማጉደፍና ቁሳዊ ጥቅሞቻቸውን ለማርካት ቤተክርስቲያኒቱን እስከመሸጥ የተሰለፉ አካላት በሕግና በቀኖና መሠረት ቤተክርስቲያን እንዳትሠራ፤ በየትኞቹም ጉዳዮች ለቁጥጥር የሚያመች ማዕከላዊ አሠራር እንዳይዘረጋ ይታገላሉ:: ይህንንም የሚያደርጉበት ምክንያት አዲስ የኑፋቄ ትምህትን አንሸራቶ ለማስገባት ለሚተጉበት እንቅስቃሴያቸው የተመቹ ሁኔታዎችን  ለመትከልና ለ«ተሐድሶ» እንቅስቃሴ አውቀውም ሳያውቁም ገፊ ኃይል በመሆን ለተሰለፉ ግለሰቦችና ቡድኖች ወረታ የሚሆን፣  ለሥጋዊ ፍላጎታቸው የሚጠቀሙበትን ንግድ በስብከተ ውንጌል ስም ለማስፋፋት ነው::

«ተሐድሶ» ቤተክርስቲያኒቱ ያላትን አሠራር በማስረጀት፣ ፕሮቴስታንታዊ አስተምህሮን ወደ ቤተክርስቲያን ለማንሸራተት ሲተጋ ለቤተክርስቲያን የሚያስፈልጋትን የአሠራር የመዋቅር እና የመፈጸም አቅም ተሐድሶ /Renaissance/  ግን ለመቅበር ይታገላል:: ቤተክርስቲያናችን በራሷ ሉዓላዊ አስተዳደር መመራት የጀመረችበት ጊዜ መቶ ዓመት ያልሞላው ከመሆኑ ጋር ተያይዞ እንዲሁም ከዚያም በኋላ የተፈጠሩ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ለውጦች ባስከተሉት ጫና በአሠራር፣ በመዋቅርና በመፈጸም አቅም በተከታታይ ሊደረጉ የሚገባቸው የእድገትና የለውጥ እንቅስቃሴዎች ሳይታሰቡ፤ ሳይተገበሩም ቆይተዋል:: «ተሐድሶ» የተባለው ይህ የመናፍቃን ተላላኪ ደግሞ አስፈላጊውን የለውጥና የማሻሻያ እርምጃ በማፈን በአውሮፓ በመካከለኛው የታሪክ ዘመን እንደተደረገው በተሐድሶ ስም ሌላ የእምነት አስተምህሮን አንሸራቶ ለማስገባት ይሠራል::

ተፈላጊውን ማሻሻያ የሚጠላበት ምክንያት ቤተክርስቲያን በአፈጻጸም ደካማ እየሆነች ስትሔድ ምናልባትም በሚያስቆጣ ደረጃ ምእመናን ያልተደራጀና ከክርስትና ሥነምግባር ውጭ የሆነ አብዮታዊ እንቅስቃሴ ውስጥ ገብተው በካህናቱ ላይ እንዲነሡ፤  ቤተክርስቲያንም እንድትበታተን ለማድረግ የታለመ ነው:: አሁንም በግልጽ እየታየ ያለው የአባቶች መወጋገዝና መከፋፈል እየጨመረ በጎጥና በዘር ላይ የተመሠረተ የተበታተነ አደረጃጀት እንዲኖር ለማድረግ ነው:: ይህንንም አሁን «ተሐድሶ» በግልጽ እየጻፈ በሚያወጣው መጻሕፍት ከእነ እገሌ ወገን ጳጳሳት ለምን አይሾሙም እያለ የሚያነሣው ከንቱ ልፍለፋ ይህን ያሳያል:: የካቶሊክ ቤተ እምነት በመካከለኛው የአውሮፓ የታሪክ ዘመን በነበረበት የጊዜውን ማኅበረሰብ ያለማርካት ችግር በተፈጠረው ተቃውሞ ቤተ እምነቱን ከሁለት የከፈለ ድንገተኛ ክስተት በ«ተሐድሶ» ስም ማስተናገዱ ይታወቃል:: በዚህ ያለው የመናፍቃን ተላላኪ «ተሐድሶ» ያንን መሰል ተከፍሎ በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ውስጥ እንዲፈጠር ያልማል:: ለዚህም ለተቃውሞ የሚያነሣሡ ብልሹ አሠራሮች በየደረጃው ባሉ የቤተክርስቲያኒቱ አስተዳደር ውስጥ እንዲሰፍን ገፊ ኃይል ሆኖ በውስጥ በሚሹለከለከው መረቡ በኩል ይጥራል:: ማኅበረ ቅዱሳን ከዚህ በፊት በመል እክቱም ደጋግሞ እንደጠቀሰው ቤተ ክርስቲያን ጠፍረው የያዙአትን ኋላቀርና ብልሹ አሠራሮች በተሻለና ሰውና እግዚአብሔርን ደስ በሚያሰኝ፣ መተማመንንና አንድነትን በሚያጸና አሠራር መተካተ እንዳለባቸው ያምናል:: ይህንን ማድረግ ካልቻልን «ተሐድሶ» «ለውጥ! ለውጥ!» በሚለው ድምፅ ውስጥ እነዚህን የአሠራር ችግሮቻችንን ሽፋን አድርጎ በግልጽ የጀመረውን ፕሮቴስታንታዊ አስተምህሮ በሒደት አንሸራቶ ማስገባት የሚችልበት እድል እንሰጠዋለን:: ስለዚህ ያሉብንን የአሠራር ውስንነቶች በሁሉም ካህናትና ሕዝበ ክርስቲያን ተሳትፎ መቅረፍና ወደተፈላጊው ትንሣኤ ልቡና መድረስ አለብን:: ለዚህም ሁሉም የክርስቲያን ወገን ሓላፊነት ቢኖርበትም የብፁዓን አባቶች ድርሻ የጎላ ነው::

ብፁዓን አባቶቻችን በታሪክ አጋጣሚ ይህ የ«ተሐድሶ» መሰሪ ኃይል በውስጥም በውጭም በተደራጀበት ዘመን ላይ ይህቺን በብዙዎች መንፈሳዊ ተጋድሎ እዚህ የደረሰች ቤተክርስቲያን ባለደራዎች ናቸው:: አባቶች ለመንጋው የማይራሩ «ተሐድሶ»ን የመሰሉ ጨካኞች በታዩ ጊዜ ሁሉ ለራሳቸውና ለመንጋው እንዲጠነቀቁ መንፈስ ቅዱስ የዘወትር ማሳሰቢያን የሰጣቸው ናቸው:: በመሆኑም ጊዜው የሚጠይቀውን የጥንቃቄ እርምጃ ከሀገረ ስብከቶቻቸው ጀምሮ እስከ መንበረ ፓትርያርክ ድረስ የሚወስዱበት፣ ለመንፈሳዊ ተጋድሎ ራሳቸውን የሚያዘጋጁበት ወቅት ነው:: ከምንም በላይ «ተሐድሶ» በአባቶችና በልጆች መካከል መለያየትን ለማስፈን የሚሠራ ከመሆኑ ጋር በተያያዘ በቤተክርስቲያን ውስጥ የሚፈጠሩ ችግሮችን ሁሉ ያሉት ብፁዓን አባቶች የመፍታተት አቅም የሌላቸው፣ ለእውነትም የመቆም ቁርጠኝነት የሌላቸው አድርጎ ስለሚያሳይ ውጤቱ ቤተክርስቲያንን መጉዳቱ ብቻ ሳይሆን የብፁዓን አባቶችን ክብርና ስብእና የሚጎዳ ሁኔታ ሊከተል ይችላል::

የ«ተሐድሶ» ግብና ዓላማ መንጋውን ከበረቱ መበተን በመሆኑ አባት የምንሆ ንላቸውን ልጆች ከማሳጣቱም ሌላ በታሪክ ተወቃሽ ሊያደርግ የሚችል ነው:: ከዚያም አልፎ በአሠራሮቻችን ድክመት  ክብረ ክህነቱ ሊጎዳ ስለሚችል «ተሐድሶ» ለሚፈልገው ሁሉም ሰው ካህን ነው ወደሚለው ፕሮቴስታንታዊ  ጸረ ሃይማኖት አቋም ያሻግራል:: ስለዚህ በቤተክርስቲያን ውስጥ ተሸሽገው ለሚሠሩ የትኞቹም ገፊ ኃይሎች እንቅስቃሴ የሚመቹ ክፍተቶችን መድፈን፤ በነገሮች ሁሉ የጸናና የተጠና ማዕከላዊ አሠራርን ማስፈን፤ የቤተክርስቲያኒቱ ቀኖናና ሕግጋት ተጠብቆ እንዲሠራ ቁርጠኛ አቋም መያዝ ይገባዋል::
ማኅበረ ቅዱሳን አባቶች እንዲረዱለት የሚፈልገውም ወሳኝ ቁም ነገር እነርሱ ጳጳሳት ሆነው የተሾሙላት ቤተክርስቲያን የሃይማኖት ትምህርት ክብርና ታሪክ ተጠብቆ፡  በብዙ ሊቃውንት ተጋድሎ ተጠብቆ ዘመናትን ተሻግሮ የተቀበልነው ማራኪ ሥርዓትም ቀጣዩ ትውልድ የማየትና የመሳተፍ እድል እንዲኖረው ማድረግ ነው:: የሃይማኖት ትምህርት በዚህ ረገድ አባቶች ለሚኖራቸው እርምጃ ሁሉ በየትኛውም መልክ ቢሆን ድጋፍ መስጠት ማኅበራችን የተቋቋመበት ዓላማ መሆኑንም ያምናል:: በመሆኑም ይህ እውን እንዳይሆን የሚታገሉ የ«ተሐድሶ» መናፍቃንን ሰርጎ ገብ የጥፋት አካሔድ ለመመከት ከአባቶች ቁርጠኛ አቋምና ተከታታይ ሥራዎች ሊኖሩ ይገባል::

ቆሞሳት ቀሳውስት ዲያቆናትና በአጠቃላይ ከብፁዓን አባቶች ቀጥሎ ሓላፊነት ያለባቸው የቤተክህነቱ ወገን ሁሉ ከአጥቢያ እስከ ጠቅላይ ቤተክህነት ባለው አገልግሎት ውስጥ የዚህች ታሪካዊት ቤተክርስቲያን ባላደራዎች እንዲሆኑ መንፈስ ቅዱስ በጳጳሳት እጅ የሾማቸው የመንጋው ጠባቂዎች ናቸው:: በመሆኑም መንጋውን ለመበተን በውስጥና በውጭ ተደራጅቶ በዓይነት ብዙ ፈተናዎችን ለማስከተል እየሠራ ያለውን የ«ተሐድሶ» የኑፋቄ ፍላጻ በመንፈስ ቅዱስ ጥበብ በጸሎት በጾም ከማምከን ጀምሮ ባልንጀሮቻችን በተለያዩ ምክንያቶች በ«ተሐድሶ» ገፊ ኃይል መረብ ውስጥ እየተጠለፉ የጥፋቱ ተባባሪ እንዳይሆኑ መጠበቅ ይገባናል:: የ«ተሐድሶ» እንቅስቃሴ በዋናነት ምስጢረ ክህነትን የሚክድ፣ ሁሉን እንደ ካህን የሚቆጥረውን ፕሮቴስታንታዊ አስተምህሮ አንሸራቶ የማስገባት ፍላጎት ያለው መሆኑን በግልጽ በሚጽፋቸው መልእክቶች መረዳት ይቻላል:: በመሆኑም «ተሐድሶ» በተባለው የመናፍቃን ተላላኪዎች ተንኮል በሃይማኖት፣ በአካልም ሆነ በሥነልቦና የመጀመሪያው ተጎጂዎች የቤተክህነቱ ወገኖች መሆናቸው አሌ የማይባል ነው:: ስለዚህ በየደረጃው ባሉ የቤተክርስቲያናችን የአስተዳደር መዋቅሮች የሚፈጠሩ ችግሮች ዘገምተኛና ስልታዊ ያልሆኑ ኋላቀር አሠራሮች ሌሎችም ችግሮች የሚያስከትሉብንን ተጽእኖዎች ተስፋ ሳያስቆርጡን ወደተሻለ አሠራር ለመግባት  እየጣርን የእነዚህን መናፍቃን የውስጥና የውጭ እንቅስቃሴ በእግዚአብሔር ረድኤት በብቃት መቋቋም አለብን:: ፈተናውንም ልንሻገረው ይገባል:: ቤተክርስቲያኒቱ ያላትን ሀብት ስልታዊ በሆነ መንገድ ማኅበረ ካህናቱንና ከዚያም አልፎ  ለሀገር እድገት ትርጉም ባለው መልክ ባለመጠቀም የካህናቱ ኑሮ እየተጎዳ ገዳማትና አድባራት እየተፈተኑ ቢሆንም፤ ይህንን ውስጣዊ ችግር የሚፈታ ጠንካራና ዘመናዊ የአስተዳደር መዋቅር ተግባራዊ ለማድረግ ከመታገል ጋር የ«ተሐድሶ»ን መሰሪ መረብ መበጣጠስ አለብን::

ይልቁንም የችግሮቻችን ሁሉ ምንጭ ቤተክርስቲያናችንን ለማዳከም ከአሁኑ የበለጠ ጠንካራ አሠራር ዘርግታ  ቀድሞ  ከነበራት ክብርና ታሪክ በላይ መሥራት እንዳትችል የሚፈልጉ በዓይነት ብዙ የሆኑ አጽራረ ቤተክርስቲያን በግልጽና በስውር የሚሠሩት ደባ በመሆኑ በፍጹም ክርስቲያናዊ ወንድማማችነት ተያይዘን መርዛቸውን ማርከስ አለብን:: በተለይ ከውስጥ ሆኖ ገጽታን በማጉደፍ ክርስቲያኖችን በየምክንያቱ በማስደንበር ገፍቶ ለማስወጣት የሚሠራውን የ«ተሐድሶ» ገፊ ሃይል እንቅስቃሴ ለማምከን ተባብረን መቆም አለብን:: ይህ ኃይል በጎ የሚመስሉ ገጽታዎችን ተላብሶ የሚጫዎት የጥፋት ተዋናይ በመሆኑ ከመቼውም ጊዜ በላይ ካህናት ጥንቃቄ ሊያደርጉ ይገባል:: «ተሐድሶ» በሚፈጠሩ ጥፋቶችም ሁሉ ምእመናን በካህ ናቱ እየፈረዱ፣ በጥላቻም ካህናቱን እያዩ እንዲሄዱ የማለያየት ተልእኮም ስላለው በነገር ሁሉ ጥንቃቄ ልናደርግ ይገባል:: በየመዋቅሮቻችን ያሉ አስተዳደራዊ ዘይቤዎችንም  ፈጣንና አርኪ ለማድረግ ተገቢ የአሠራር ማሻሻያ ልናደርግ ይገባል:: ለዚህም መተባበር አለብን:: ይህንን ደግሞ የግድ የሚያደርገው ወቅቱ ነው:: ወቅቱ ግድ የሚለን «ተሐድሶ» እንደሚለው ሃይማኖታችንን እንድንለውጥ ሳይሆን በዚህ ጊዜ ውስጥ ሃይማኖታችንን የምናስተምርበት፣ የምናጸናበት፣ ያሉንን ሥርዓተ አምልኮ ለቀጣዩም ትውልድ የምናስተላልፍበትን የተሻለ አስተዳደራዊ ሁኔታ ማስፈን ነው:: ለዚህም ካህናት ሁሉ ሊተባበሩ ይገባል እንላለን::

ሰንበት ትምህርት ቤቶችም «ተሐድሶ» ቤተክርስቲያኒቱን ለማዳከም መሣሪያ ሊያደርጋቸው የሚፈልጋቸው የቤተክርስቲያኒቱ የአገልግሎት ተቋማት ናቸው:: በመሆኑም ይህንን ደባ ከማክሸፍ አንጻር የአገልግሎት አሰጣጣቸውን እየቃኙ ወደ ከፍተኛ የስብከት ወንጌል መድረክነት ሊለወጡ ይገባል:: ሰንበት ት/ቤቶች መረዳት ያለባቸው ወሳኝ ነጥብ የአገልግሎት አሰጣጣችን ወደሚፈለገው ደረጃ አለማደግ በምእመናን ዘንድ ከፍተኛ የቃለ እግዚአብሔር ጥማት ይፈጥራል:: ይህ ደግሞ የራሳቸውን ንግድ ሊያጧጡፉ ለሚፈልጉ አንዳንድ ሰባክያንና ዘማርያን በር ከፍቷል::«ተሐድሶ» ፕሮቴስታንታዊ አስተምህሮን አንሸራቶ በማለማመድ ሊያስገባበት የሚፈልገው ክፍተት ይህ ነው::ስለዚህ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ከነበረው በተሻለ አፈጻጸም ውስጥ ሊገኙ ይገባል:: በአጥቢያ ቤተክርስቲያናቸው ውስጥ የሚደረጉ የትኞቹንም እንቅስቃሴዎች የመከታተል፣ የአጥቢያውን ሰበካ ጉባኤ በሚያከናውናቸው መንፈሳዊና ልማታዊ ተግባራት ውስጥ ድጋፍ መስጠት የአጥቢያውንም ምእመናን ማስተባበር በአጥቢያው ውስጥ እንግዳ ትምህርትና ተገቢ ያልሆኑ ሥርዓቶችን ለማስረግ የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን በግልጽ የመቃወም ሓላፊነትም አለባቸው:: አሁን አሁን በአንዳንድ ጠንካራ ሰንበት ትምህርት ቤቶች እንደሚደረገው የአብነት ትምህርቶችን ለሕፃናትና ወጣቶች በመስጠት፣ ካህናትን የሚደግፉና የሚተኩ ወጣቶችን ማፍራት፣ ወቅቱን የሚዋጅ አጽራረ ቤተክርስቲያንን የሚያስታግስ ተከታታይ ትምህርቶችን አርኪ በሆነ መንገድ በዓይነትና በደረጃ ለይቶ መስጠት፣ ስልታዊ በሆኑ የመረጃ ቅብብሎሽ እየታገዙ የ«ተሐድሶ»ን ገፊና ጎታች ኃይል እንቅስቃሴ ለመግታት መተባበር አለባቸው:: በተለይ ወቅቱ ተራ በሆኑ የወጣትነት ስሜቶች የምንዘናጋበት ባለመሆኑ ቤተክርስቲያን ለዚህ ትውልድና ለዚህች ሀገር ማበርከት ያለባትን አስተዋጽኦ ማበርከት እንድትችል የማያቋርጥ ተሳትፎ ልናደርግ ይገባል::

ማኅበራትም ለቤተክርስቲያኒቱ አገልግሎት በተለያየ መንገድ ድጋፍ ለማድረግ የተቋቋሙ በመሆናቸው፡ የ«ተሐድሶ» ሤረኛ እንቅስቃሴ ሰለባና ተባባሪ እንዳይሆኑ ሊጠነቀቁ ይገባል:: ማኅበራት ከመገንባት ይልቅ አፍራሽ በሆነ መንገድ ላይ ሳያውቁት እንዳይቆሙ የሚችሉትን ያህል ጥንቃቄ እያደረጉ ለቤተክርስቲያኒቱ አንድነት መሥራት አለባቸው::በተቻለ መጠን ቤተእግዚአብሔርን ማገልገል የሚፈልጉ የተለያዩ ማኅበራትን ማስተባበር የምትችልበትን አቅም ቤተክርስቲያን አግኝታ፣  ጠንካራ ማዕከላዊ አሠራር ሰፍኖ ተቀናጅተን መሥራት የምንችልበት ሁኔታ እንዲፈጠር ልንተጋ ይገባል:: የማኅበሮቻችን አባላት በውስጥና በውጭ ተደራጅቶ ቤተክርስቲያንን ለማዳከምና ለማፍረስ የሚጥረውን የ«ተሐድሶ» ተንኮል ነቅተው ሊከላከሉ፤ ለዚያ የተንኮል ሥራው ምቹ ሆነው የሚንቀሳቁ ግለሰቦችንና ቡድኖችን ሊመክሩና ሊያስተካክሉ ካልሆነም ሊለዩ ይገባቸዋል እንላለን::

ምእመናን የዚህች የእግዚአብሔር የጸጋ ግምጃ ቤት በሆነች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመንፈስ ተወልደው በቃሉ ወተት እያደጉ ያሉ፤ የአገልግሎቱ ደጋፊ፣ ተቀባይ፣ ተሳታፊም በመሆናቸው ቤተክርስቲያን ማለት እነሱ ራሳቸው እንደሆኑ መረዳት ይገባቸዋል:: አባቶቻችን የእግዚአብሔር ቤተክርስቲያን ሆኖ ለመባረክ ክርስቶስ ያደረገልንን ማዳንም አምነው፤ በየዘመናቱ የምንነሣ እኛ ልጆቻቸውም በዚያ ጸንተን ለቀጣዩም ትውልድ ባለአደራ እንድንሆን አድርገዋል:: ይህንን ሓላፊነት የተረዱ በየዘመኑ የተነሡ ምእመናን እስከ ሕይወት መስዋዕትነት ድረስ ዋጋ በመክፈል ቤተክርስቲያናቸውን ሊያፈርስ ከመጣ የዲያብሎስ ሠራዊት ጋር ተጋድለዋል:: አሸናፊም ሆነዋል:: በዚህም ምክንያት ምዕተ ዓመታትን ተሻግሮ የመጣን ማራኪ ሥርዓተ ቤተክርስቲያን፣ ሕይወትን የሚሰጥ ሃይማኖትን ለማየትና ለመመስከር በቅተናል:: የያሬድን ዜማ፣ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫን ሰዓታት የበርካታ ሊቃውንትን ትምህርትና ቅዳሴ የመስማት እድል አግኝተናል::

ይህንን እድል ለቀጣዩ ትውልድ የማስተላለፉ አደራ በእኛ ትውልድ ላይ በወደቀበት በዚህ የታሪክ አጋጣሚ ውስጥ ደግሞ በቀጣዩ ትውልድ ውስጥ በሚሰበሰበው መንጋ ላይ መጨከን የለብንም:: በየዘመናቱ ቤተክርስቲያንን ከአገልግሎት ለማዘግየት የሚወረወረው የሰይጣን ፍላጻ ዓይነቱ ይለያይ እንጂ ይኖራል:: አባቶቻችንም በእግዚአብሔር ረድኤት ያ ፍላጻ ቤተክርስቲያንን ከአገልግሎት እንዳያስተጓጉላት ዋጋ ከፍለዋል:: አሁን ደግሞ ከውስጥም ከውጭም የሚንበለበል «ተሐድሶ» የተባለ ፍላጻ እየወጋን ይገኛል:: የዚህ ሁሉ ውጊያው ዓላማ እናንተን ምእመናንን ከመንጋው ኅብረት ለይቶ ለምድ ለለበሰ ተኩላ ለመስጠት፤ ከተቻለም ራሳቸው ምእመናን የምታገለግላቸውን ቤተክርስቲያን በማጥፋቱ ሒደት እንዲሳተፉ ለማድረግ ነው:: ስለዚህ ምእመናን በዚህ አካሔድ ላይ በመንቃት ጥንቃቄ በተሞላበት እርምጃ ውስጥ እንድንገባ ያስፈልጋል:: በተለይ ትኩረት የሚስቡ የተለያዩ ሁኔታዎችን በስብከተ ወንጌል አገልግሎት ሒደት ውስጥ በማስገባት ብዙ መንጋ ከሰበሰቡ በኋላ ገንዘቡን  ከመብላት አልፈው በሒደት አዲስ ትምህርትን አምጥቶ በማለማመድ ወደ ፕሮቴስታንታዊ አስተምህሮ ማንሸራተት ይፈልጋሉ:: በዚህም ግማሹን መንጋ ይዞ ለመንጎድ ቀውንም በመምህራንና ዘማርያን ላይ እምነት በማሳጣት በቤተክርስቲያኒቱ የትኛውም የስብከተ ወንጌል ማዕድ ላይ እንዳይሳተፉ ለማድረግ ነው:: በመሆኑም ምእመናን ክርስቶስን ትኩር ብሎ ከማየት አዘንብለው በዓለም እንዳለው የግለሰቦች ዝና ገንቢና ሳያውቁት ለሥጋዊና ቡድናዊ ፍላጎታቸው መጠቀሚያ እንዳይሆኑ፤ ብሎም ውሎ አድሮ ለሚያስከትሉት ቤተክርስቲያንን የማዳከም ዘመቻ ተባባሪ እንዳንሆን ልንጠነቀቅ ይገባል:: ቤተክርስቲያን በአገልግሎት ሒደት ውስጥ ያሉባት ክፍተቶች እንዲሞሉ በጸሎት ከመትጋት ጋር የ«ተሐድሶ» ዘርፈ ብዙ ወጥመድ ለመበጣጠስ መቆም አለብን::
በአጠቃላይ «ተሐድሶ» ትናንት ሲያደርግ የነበረውን የተላላኪነት ሤራ ተልእኮ የሰጡት አካላት የሚሰጡትን የገንዘብና የቀሳቁሰ ሰፊ ድጋፍ በመጠቀም ከውጭ ፈሪሳዊ በሆነ መንገድ ከውስጥ ይሁዳዊ በሆነ ስልት ለመዝመት እየጣረ ነው:: ሰይጣን በርካታ ጠላቶችን በቤተ ክርስቲያናችን ላይ እያዘመተ ቢሆንም ከውጭ ያለውን ለማስታገስ እንዳትችል አንቆ የያዛትን የ«ተሐድሶ»ን መሰሪ ኃይል መለየትና በቤተክርስቲያናችን ውስጥ አገልግሎቱን በቅልጥፍና የሚመራ አስተዳደራዊ ትንሣኤ እንዲኖር ማድረግ ግን ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ መሆኑን ማኅበረ ቅዱሳን የጸና እምነት አለው:: ጉዳዩም የህልውና ጉዳይ መሆኑን ያምናል፡፡ ዋጋ ሊያስከፍል እንደሚችልም ያስባል:: ነገር ግን በተናጠልም ይሁን በኅብረት ክርስቲያናዊ ግዳጃችንን መወጣት ለነገ የማይባል ነው:: የራሳችንን ቤተክርስቲያን እንዳንጠብቅ የሚከለክለን ወይም በቁማችን ዓይናችንም እያየ ስትፈርስ እዩአት የሚለን አካል አለ ብለን አናምንም:: ምክንያቱም ቤተክርስቲያኒቱ ወልድ ዋሕድ ብለው የሚያምኑ፣ የቤተክርስቲያኒቱን ቀኖናና ሕግ ጠብቀው፣ አስከብረው የሚሔዱ ብፁዓን አባቶች፤ ቀን ከሌሊት በሚሰጡት የማያቋርጥ አገልግሎት መንጋውን የሚጠብቁ ካህናት፤ በዝማሬ በውዳሴ የሚተጉ ሰንበት ተማሪዎች፤ ሕይወት የሚያገኙባትን ኅብረት በሚሰጡት ዐሥራት በኩራት የሚጠብቁ ምእመናን ቤተክርስቲያን ነችና:: በተለይም ቅጥረኛ ሆኖ በውስጣችን ለመሸመቅ የሚጥረውን ጨካኝና መሰሪ የ«ተሐድሶ» እንቅስቃሴ መታገስ የማይቻል ነው:: ክቡር ዳዊት «ጠላትስ ቢሰድበኝ በታገስሁ ነበር፤ የሚጠላኝም አፉን በላዬ ከፍ ከፍ ቢያደርግ ከእርሱ በተሸሸግሁ ነበር፤ አንተ ሰው አንተ ግን እንደራሴ ነበርህ» /መዝ.4÷02/ እንዳለ የ«ተሐድሶ» ፍላጻ ከውስጥ የሚወረወር በመሆኑ የከፋ ነው:: ስለዚህ እኛ ሁላችን ቤተክርስቲያናችንን ተባብረን የመጠበቅ ሓላፊነት አለብን::  ማኅበረ ቅዱሳን በዚህ ረገድ ያለበትን ሓላፊነት በእግዚአብሔር ረድኤት ከሚመለከታቸው ሁሉም አካላት ጋር በመመካከር በተከታታይ ለመወጣት ያለውን ዝግጁነት በዚሁ አጋጣሚ ለመግለጽ ይወዳል::

                                                   ምንጭ፡ ሐመረ ተዋሕዶ ነሐሴ 2002 ዓ.ም.

ለእውነት እንጂ በእውነት ላይ ምንም ለማድረግ አንችልም

በአሁኑ ዘመን ዓለማችን በከፍተኛ የአስተሳሰብ፣ የቴክኖሎጂና የማኅበራዊ ለውጥ ሒደት ውስጥ ትገኛለች፡፡ እነዚህን የለውጥ ሒደቶች  የመረዳት አቅም ያጣ ግለሰብም ሆነ ተቋም የሚሻውን በቀላሉ መፈጸምና ማስፈዐም አይችልም፡፡  አላማዎቹ በጎም ይሁኑ ክፉ ከተጨባጭ ሁኔታዎቹ ተነጥሎ ማሳካት አይችልም፡፡ በሀገራችንም ከመንግሥት ጀምሮ በርካታ ድርጅቶች ከሙከራ ትግበራ አንሥቶ ሀገር አቀፍ አፈጻጸም እስኪሆኑ ድረስ እነዚህን ሁኔታዎች ያገናዘቡ የተለያዩ የአሠራር ማሻሻያዎችን ተግባራዊ እያደረጉ ነው፡፡
ቅድስት ቤተክርስቲያናችንም በዚህ ዓለም ያሉ የለውጥ ሁኔታዎችን ከግምት በማስገባት ለጊዜያችን የሚመጥን፣  የተቀበለችውን የእግዚአብሔርን መንጋ የመጠበቅ ሐላፊነቷን መወጣት የሚያስችላት፣ ከክርስቶስ ፍቅር የማይለይ አሠራርን በአመራርና አስተዳደራዊ ክፍሎቿ ማስገባት ግዴታዋ ሆኗል፡፡ ግዴታውን ያስከተለው ደግሞ ሰው ሳይሆን አጠቃላይ ዓለማዊ ሆኔታው ነው፡፡ ይህ ለውጥ ደግሞ የማይካድ እውነት ነው፡፡ ለዚህ እውነታ መሥራት ደግሞ ተገቢም አስፈላጊም ነው፡፡
ክርስቲያኖች አነሰም በዛም የጊዜውን የአሠራር ለውጥ ሒደት እያፋጠነ ያለው የመረጃ ቴክኖሎጂ ተጠቃሚዎች እየሆኑ ነው፡፡  የመረጃ ቴክኖሎጂው ደግሞ ክርስቲያኖች ክፉና ደጉን እንዲያውቁ ለማድረግ እገዛ አድርጎላቸዋል፡፡ ከዚያም አልፎ የእነሱ የሆነውን ከሌሎች ጋር ማነጻጸራቸው አይቀሬ ነው፡፡ ቤተክርስቲያን ደግሞ የክርስቲያኖች ነች፡፡ ስለዚህ የእኛ ብለው ላመኑባት ቤተ ክርስቲያን በጎውን እንድትይዝ፣ ከክፉው እንድትሸሽ ይመኛሉ፤ ለሚመለከተው ያሳስቡበታልም፡፡ ለዚያም ይሠራሉ፡፡ ይህም ሌላው እውነታ ነው፡፡

ምእመናን ይህን ወቅታዊ የለውጥ ሒደት ከግምት አስገብተው ቤተክርስቲያናቸውን ከመጠበቅ አንፃር ዛሬ ይዛ እንድትገኘ ከሚፈልጉአቸው ዋና ዋና ጉዳዮች አንዱ የአመራርና አስተዳደራዊ አቅምን የማጠናከር ተግባርን ነው፡፡
የአመራርና አስተዳደር አቅም ማለት ደግሞ የአሠራር፣ የአደረጃጀትና የሰው ኃይል አቅምን ይመለከታል፡፡ ያለን አሠራር ከነቀፋ የሚያድነን፣ ለመተማማት ሰበብ የማይፈጥር /ግልጽ/ ያጠፋ የሚቀጣበት፣ ያለማ የሚከብርበት /ተጠያቂነት የሰፈነበት/ እንዲሆን ነባራዊ ሁኔታው ያስገድዳል፡፡ ለዚህም ከሕገ ቤተክርስቲያኑ ጋር የማይጋጭ፣ በየደረጃው ያሉ የሥራ ክፍሎችን እርምጃ የሚያፋጥን ደንብና መመሪያ አዘጋጅቶ ማጽደቅ ይፈልጋል፡፡  ይህ ደግሞ ያለንን መዋቅርና አደረጃጀት እንድንፈትሽ ይጠይቃል፡፡ አካባቢያዊ ለውጦችን ከግምት አስገብቶ በዘመናዊው የአስተዳደር ዘይቤ የሚመራ የሰው ኃይል በየደረጃው መቀመጥ ይኖርበታል፡፡ እነዚህ ግፊቶች የተወሰኑ ግለሰቦች ወይም ቡድኖች ያመጡት አይደለም፡፡ የአጠቃላዩ የለውጥ ግስጋሴ ያስከተላቸው ናቸው፡፡ ከላይ የተጠቀሱትን ነጥቦች በየጊዜው ከሚፈጠሩ ሁኔታዎች ጋር በማስተያየት፣ ነባር፣ ጠቃሚና መንፈሳዊ የሆኑ፤ መቼም መች የሚያስፈልጉንን ኦርቶዶክሳዊ መገለጫዎቻችንን ከመጠበቅ ጋር እያጣጣሙ ማካሔድ ለነገ የማይባል ተግባር ነው፡፡ በፍጥነት ተግባራዊ እንድናደርግ ያስገደደንም ከላይ የጠቀስናቸው ተጨባጭ እውነታዎች ናቸው፡፡ ለዚህ እውነታ ደግሞ ማድረግ ያለብንን እንድናደርግ ያስፈልጋል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስም እነዚህን የምእመናንን ትኩረቶች ተረድቶ በቅርቡ የአመራርና አስተዳደራዊ አቅምን ለመገንባት ወይም የተሻሉ ጠቃሚ ለውጦችን ለማምጣት ያሳየው ፍላጎትና ጅምር እንቅስቃሴ የሚበረታታ ነው፡፡  «ቀኖቹ ክፉዎች ናቸውና ዘመኑን ዋጁ» ያለውን የሐዋርያውን ምክር ሰምቶ እነዚህን ጅምር እንቅስቃሴዎች መደገፍ ደግሞ የክርስ ቲያኖች ሁሉ ድርሻ ነው፡፡

ይሁን እንጂ እነዚህን ተፈላጊ ለውጦች ለማምጣት የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች አልጋ በአልጋ ሆነው እንደማይሔዱ በቅርቡ የተከሰተው ውጣ ውረድ አመላካች ነው፡፡ይሁንና የቤተክርስቲያኒቱን አንድነትና የቅዱስ ሲኖዶስን የሥልጣን የበላይነት ከማስጠበቅ ጋር ተገቢ ለውጦችን አቅዶ መተግበርን ጊዜው የማይቀር አድርጎታል፡፡ የአሠራር ማሻሻያዎችን ለማምጣት በሚደረጉ የውይይት ሒደቶች በቅዱስ ሲኖዶስ አባላት  መካከል የተለያዩ አስተያየቶች ቢከሰቱ እንኳን ልዩነቶቹ ሊከበሩ ይገባል፡፡ ለመግባባት የሚያስችሉ፣ በበጎ ሐሳብ የሚፈጸሙ ተከታታይ ውይይቶችን ማድረግ ግን አስፈላጊ ነው፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት የሆኑ አባቶች ሁሉ ፍላጎት ለራስ ሳይሆን ለቤተክርስቲያን እስከሆነ ድረስ የአስተያየት ልዩነቶች ቢንፀባረቁም ከብዙኃኑ ብፁዓን አባቶች ውሳኔ ለመለየት አያበቃም፡፡ የራስ ፍላጎቶች እየገነኑ ከመጡ ግን መለያየትን ይጋብዛሉ፡፡ መጽሐፍም «መለየት የሚወድ ቢኖር ምኞቱን ይከተላል» እንዳለ፡፡

ሁሉም የቅዱስ ሲኖዶስ  አባላት  ለሺሕ ዘመናት ብዙ ውጣ ውረዶችን እያለፈች ለኢትዮጵያና ለዓለም ሕዝብ ጭምር እንደብርሃን የሚታዩ በጎ ተግባራትን ስትፈጽም የኖረችው ቤተክርስቲያን ባለአደራዎች እንደሆኑ እናምናለን፡፡  አባቶች ይህንን ተረደተው በስውርም ይሁን በግልጽ፣ በግልም ይሁን በቡድን የሚፈጸሙ ጣልቃ ገብነቶችን ተቋቁመው እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለጊዜያችን የሚያስፈልገውን የአመራርና የአስተዳደር ዓይነትና ደረጃ በቤተክርስቲያን ማስፈን አለባቸው የሚል እምነት አለን፡፡ ለዚህ ደግሞ የተጠሩለትን ሕይወትና ዓላማ ከመረዳት ጀምሮ እውነትን ለማገልገልና ለዚያም መከራ አስከመቀበል ለመትጋት ቁርጠኝነት ይጠይቃል፡፡ ለሚገባና እውነት ለሆነው ነገር መከራን መቀበል የሚገባ ነውና፡፡

በዓለም ያሉት ለውጦች ደግሞ ተጨባጭ ስለሆኑ ለእነዚህ እውነታዎች ተገቢውን ምላሽ በመስጠት ረገድ የሚኖረን ቁርጠኝነትም ከመለያየት ይልቅ ያቀራርባል፡፡ ያሉትን የለውጥ ሒደቶች፣ የክርስቲያኖችን በጎ ፍላጎት ካልካድን በስተቀር በእርግጠኝነት የአሠራር ማሻሻያዎችን የተጠየቅንበት ጊዜ አሁን ነው፡፡ ያሉት ሁኔታዎች እውነት ናቸውና ለእው ነት በእውነተኛ መንገድ ማገልገል አለብን፤ ሐዋርያው እንዳለው «በእውነት ላይ ምንም ለማድረግ አንችልምና፡፡» ስለዚህ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ዛሬም ይሁን ነገ በግልና በቡድን በሚፈጸሙ የጨለማ ሥራዎች ሳይደናገጡ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ለመፈጸም ተገቢውን አሠራር  እውን ለማድረግ በረድኤተ እግዚአብሔር እንደሚንቀሳቀሱ እምነታችን ነው፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ በምልዓተ ጉባኤው አሉ ብሎ ያስቀመጣቸውን በአመራሩና በአሰተዳደሩ የታዩ ችግሮችን ካልፈታና መፍታት የሚያስችሉ ግልጽነትና ተጠያቂነት የሰፈነባቸው አሠራሮችን ለመዘርጋት ቁረጠኝነት ካጣ ቤተክርሰቲያን በሒደት ሊገጥማት የሚችለው ፈተና ማኅበረ ቅዱሳንን በእጅጉ ያሳስበዋል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ በምልዓተ ጉባኤው በቤተ ክርስቲያኒቱ ተንሰራፍተዋል ያላቸውን የአሠራር ችግሮች ግልጽ ካደረገበት ጊዜ ጀምሮ ቤተክርስቲያኒቱ በሁለት ተገቢ ባልሆኑ የአካሔድ አጣብቂኝ ውስጥ እንዳትወድቅ ማኀበራችን  ስጋት አለው፡፡ አንደኛው ቅዱስ ሲኖዶስ በምልዓተ ጉባኤው ግልጽ ያደረገው የውስጥ አሠራር ችግር ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ እነዚህን የአሠራር ችግሮች አጋኖ በማራገብ ቤተክርስቲያኒቱን በቅጥረኛነት ለማጥፋት የሚካሔደው የተሐድሶ እንቅስቃሴ ነው፡፡ ከዚህ አጣብቂኝ ሌላ በሚኖሩ ኋላቀርና ብልሹ አሠራሮች በመመረር ምእመናን የተለያየ አደረጃጀት ፈጥረው በራሳቸው ማስተዋል በመንቀሳቀስ ለቤተክርስቲያን መከፋፈል ምክንያት ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ እንዲሁም የያዝነውን ደካማ አሠራር የጠሉ በመንፈስ ያል ጠነከሩ ምእመናን ይሰናከላሉ፡፡ ሥራዎቻችንን ከሚሠሩበት መሥሪያ ቤት፣ ካላቸው ድርጅት ተሞክሮ፣ ከሌሎች አኀት አብያተ ክርስቲያናት ዕድገትና ግስጋሴ ጋር የሚያስተያዩት ደግሞ የአመራርና የአስተዳደር ዘይቤያችንን በመናቅ ይለዩናል፡፡ ከዚያም አልፎ የቤተክርስቲያኒቱ ቅርስ፣ ሀብትና አስተዳደር በአጽራረ ቤተክርስቲያን እጅ እስከ መያዝ ሊደርስ ይችላልና፡፡ ቤተክርስቲያን የማትሸነፍ ቢሆንም የብዙ ምእመናን ሕይወት መፈተኑ የማይቀር ይሆናል፡፡

ማኀበራችን ደግሞ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ እስካሁን ድረስ ሲንቀሳቀስ የነበረው ቤተክርስቲያን ይህ እንዳይገጥማት ነው፡፡ ስለዚህ ያሉ እውነታዎችን ያገናዘበ ችግር ፈቺ አሠራር እንዲዘረጋ ይፈልጋል፡፡ የምንጊዜም ፍላጎቱ ይህቺን ታሪካዊ፣ ሐዋርያዊና ቅድስት ቤተክርስቲያን ያሉአትን ትውፊት፣ ቅርስና አስተምህሮ ጠብቆ የሚያቆይ የአመራርና የአስተዳደር ሥርዓት እንዲኖራት ብቻ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በአቢዮት ሳይሆን ሓላፊነት ያለበት ቅዱስ ሲኖዶስ በሚሰጠው አቅጣጫ መሠረት በተገቢ ባለሙያዎች በተጠና መንገድና ከመቼውም ጊዜ በላይ በፍጥነት ተግባራዊ እንዲሆን ይፈልጋል፡፡   

በመሆኑም የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት አባቶች  ለዚህ ትውልድ የደረሰችው ቤተክርስቲያን ወሳኝ ባላደራነታቸውን ተረድተው ከቀደሙት አባቶቻቸው ቆጥረው ሰፍረው የተረከቡትን የቤተክርስቲያኒቱን መንፈሳዊና ቁሳዊ ሀብት ለተተኪው ትውልድ በአግባቡ ማስረከብ ይገባቸዋል፡፡ ለዚህም ይህንን ለማድረግ የሚያስችል ኦርቶዶክሳዊና ዘመናዊ አስተዳደርን የማስፈን ሐላፊነታቸውን በሰከነና አሳማኝ በሆነ አካሔድ እንደሚፈጽሙ እምነታችን ነው፡፡ ይህንንም ስንል ያንን በማድረግ ሒደት የሚኖሩ የተለያዩ አስተያየቶችም አንዱን አሸናፊ ሌላውን ተሸናፊ አደርጎ ከማሳየት ይልቅ በየጊዜው ከሚኖሩ ለውጦች ጋር እየተፈተሹ የሚተገበሩ የአካሔድ ዓይነቶች ተደረገው መወሰድ እንዳለባቸው ከመጠቆም ጋር ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም ሕገ ማኅበሩን አጽድቆ የሥራ ፈቃድ የሰጠው ቅዱስ ሲኖዶስ እነዚህን ተፈላጊ የአሠራር ማሻሻያዎች ለማምጣትና ተግባራዊ ለማድረግ በሚደረገው እንቅስቃሴ ውስጥ የሚሰጠው ሓላፊነት ካለ ለመወጣት ዝግጁ መሆኑን በዚሁ አጋጣሚ ይገልጻል፡፡  

ማኅበራትና ሰንበት ትምህርት ቤቶችም አባቶቻችን የሚያደርጉአቸውን የለውጥ ምክክሮች በበጎ በመመልከት ለጊዜያችን የሚገቡና አላራመድ ላሉን ለቤተክርስቲያናችን ችግሮች መፍትሔ የሚሆኑ የአመራርና የአስተዳደር አቅም ግንባታ እንቅስቃሴዎቹ ተጨባጭ እስኪሆኑ ድረስ ከቅዱስ ሲኖዶስ ጎን መቆማችን ተገቢ እርምጃ ነው፡፡ የአመለካከት ልዩነቶች ቢኖሩ እንኳን እነዚህን ሁኔታዎች እንደዕድል ተጠቅመው መለያየትና ማሰናከያን የሚያደርጉ ግለሰቦችና ቡድኖችን ለማስታገስ መረባረብ ይገባናል፡፡
በአጠቃላይ ምእመናን እግዚአብሔር አስቀድሞ የሰበሰባትን፣ ኋላም ከብዙ መከራ ታድጐ እዚህ ያደረሳትን ቤተ ክርስቲያን አሁንም እንዲጠብቅልን በጸሎት መቆም ይገባናል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተክርስቲያኒቱን አመራር ለስብከተ ወንጌልና ለልማታዊ ተግባራት በሚመች መልኩ ለመቃኘት የሚያደርገውንም እንቅሰቃሴ እንድንደግፍ፤ ያንንም ለማኮላሸት የሚደረጉ ስውርና ግልፅ የሆኑ ሕገወጥ አካሔዶችን ሥርዓተ ቤተክርስቲያን በሚፈቅደው አግባብ ለማስቆም አንድንጥር ማኅበራችን ይጠይቃል፡፡
 
                                                             ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የቅዱስ ሲኖዶስ ሰማያዊና ሉዓላዊ ሥልጣን ይከበር!

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም የሐዋርያትን ሥልጣን የያዘ የራሷ ቅዱስ ሲኖዶስ ባለቤት ከሆነች እነሆ ሃምሳ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶሱም በሐዋርያት መንገድ አካሔዱን አጽንቶ ለመገኘት የራሱን ሕገ ቤተ ክርስቲያን አዘጋጅቶ ተቋማዊ አመራሩን ለማጠንከር ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ በዚህም ሕገ ቤተ ክርስቲያን የቅዱስ ሲኖዶሱ፣ የቅዱስ ¬ትርያርኩ፣ የቋሚ ሲኖዶስ፣ የመንበረ ¬ትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ሥራ አስኪያጅ፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፣ የሊቃነ ጳጳሳትና የአስተዳደር ጉባኤው … ሥልጣንና ተግባር በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ በግልጽ ተቀምጧል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስም የሕግ አውጪው አካል እርሱ በመሆኑ ለጊዜው በሚያስፈልጉና ወቅቱ በሚጠይቃቸው አግባቦች የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን ጥንካሬ ለማስጠበቅና ከቤተ ክርስቲያን ጠላቶች ጠብቆ፤ ለቀጣይ ትውልድ ከመንፈስ ቅዱስ የተቀበለውን አደራ ለማስረከብ ያወጣቸውን ሕግጋት ያስጠብቃል፤ ያሻሽላልም፡፡ ለሚያወጣቸውም ሕግጋትና ለውሳኔዎቹ መነሻ የሚሆኑት ደግሞ ቅዱሳት መጻሕፍትና የመንፈስ ቅዱስ ጸጋና ረድኤት ናቸው፡፡ ያሉ ችግሮችንም አጉልተው ሊያሳዩ የሚችሉ እውነተኛ መነጽሮቻችን እነርሱ ናቸውና፡፡

ይሁን እንጂ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በቅዱስ ሲኖዶስ አሠራር ውስጥ ጣልቃ የሚገቡና ካለው ሕግና ሥርዓት ውጪ የሚንቀሳቀሱ ግለሰቦችና ቡድኖች እየተስተዋሉ ነው፡፡ ለዚህም ማሳያው ከግንቦት 5 እስከ 13 ባደረገው ጉባኤ ያሳለፈውን ውሳኔ ተከትሎ የተከሰተው ችግር ነው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ በቤተ ክርስቲያኒቱ ታይቷል ያለውን «የአስተዳደር ችግሮች፣ የሙስናና፣ የቤተሰባዊ አስተዳደር» አካሔድ መኖሩን በማመን ዘመኑን የዋጀ በተጠና ዕቅድና አፈጻጸም የሚከናወን፤ ሓላፊነትና ተጠያቂነት የሰፈነበት ዘመናዊ የአስተዳደር ሥርዓት ለመዘርጋት ውሳኔ አስተላልፏል፡፡ በውይይቱም ወቅት በአሠራሮች ውስጥ የመልካም አስተዳደር፣ የፋይናንስ አጠቃቀም፣ የሰው ኃይል አደረጃጀት ችግሮች መታየታቸውንና በልማት ሥራዎችም የሚፈለገውን ያህል ለውጥ አለመኖሩ ላይ ከስምምነት ደርሷል፡፡ እነዚህን ችግሮች ለማስተካከልና ከእርሱ የሚጠበቀውን የቅድስና አሠራር ለማስፈን የሚያስችል ከብፁዓን አባቶች የተውጣጣ ኮሚቴ የሰየመ ቢሆንም ተግባሩን ለማከናወን ያደረገው ጅምር እንቅስቅሴ ግን ውዝግብ አስከትሏል፡፡ ለዚህ ችግር መፈጠር ደግሞ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረጉ ያሉት ከብፁዓን አባቶች ውጪ ያሉ ግለሰቦች መሆናቸው በተከታታይ እየሆኑ ያሉት ነገሮች ያመለክታሉ፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ይጠቅማል በማለት የወሰነው ውሳኔ ገና ተግባራዊ እንቅስቅሴ ሳይጀመርበት አለመግባባት እንዲከሰት የሚንቀሳቀሱ ኃይሎች ማንነት ደግሞ አጠያያቂ ሆኗል፡፡ ምክንያቱም የውሳኔው አተገባበር ገና በሒደት ላይ እያለ ይህ ዓይነት ውዥንብር እንዲፈጠር መፈለጉም ማኅበራችንን ጨምሮ ለብዙ ምእመናን ያሳዘነ አካሔድ ሆኗል፡፡

ከዚህ አልፎም የቤተ ክርስቲያኒቱን አባቶች ክብርና ስም የሚያጐድፍ ተያይዞም የቤተ ክርስቲያንን እውነተኛ መንገድ የሚያሰድቡ የሕትመት ውጤቶችን በማሠራጨት የብፁዓን አባቶችን እንቅስቅሴ ለማዳከም፣ ለስምና ለክብራቸው በመሰቀቅ መልካሙን እንዳይሠሩ ለማድረግ የተለያዩ አፍራሽ እርምጃዎች ተወስደዋል፡፡ ከቅዱስ ¬ትርያርኩ ጀምሮ ብፁዓን አባቶች በሚያጠፉት ጥፋት ጠያቂ፣ ከሳሽ፣ ፈራጅ፣ መካሪ … ራሱ ቅዱስ ሲኖዶስ ሆኖ ሳለ ከዚያ አግባብ ውጪ፣ ከክርስቲያኖች በማይጠበቅ መንገድ፣ ለቤተ ክርስቲያን በመቆርቆር ስም የሚደረጉ የጥፋት ዘመቻዎች መቆም እንዳለባቸው ማኅበራችን የጸና እምነት አለው፡፡

በመሆኑም ቅዱስ ሲኖዶስ በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ መሠረት ያለውን ሰማያዊና ሉዓላዊ ሥልጣን ራሱ የማስከበር ሓላፊነት ያለበት ሲሆን የቅዱስ ሲኖዶስ አባል የሆኑ ሁሉም ብፁዓን አባቶች የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ሁሉ ሕገ ቤተ ክርስቲያኑን ጠብቀው እየተከናወኑ መሆኑን ማረጋገጥ ይኖርባቸዋል እንላለን፡፡ ችግሮችም በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተወሰኑ ውሳኔዎችን ተግባራዊ በማድረግ ሒደት ላይ የተከሰቱ ስለሆነ የሲኖዶሱን ውሳኔ አፈጻጸም እንዲከታተል ሕገ ቤተ ክርስቲያኑ ሓላፊነት የሰጠው አካል ሓላፊነቱን እንዲወጣ ያስፈልጋል፡፡

በውሳኔ አሰጣጥ፣ ውሳኔዎችን በመተርጐም ሒደት ብፁዓን አባቶች ያላቸውን ግልጽ ድርሻ በረድኤተ መንፈስ ቅዱስ፣ በቅዱሳት መጻሕፍትና በሕሊና ምስክርነት ላይ ተደግፈው መፈጸም እንዳለባቸው የሁሉም እምነት ነው፡፡ በዚህ መንገድም አካሔዱን ካላጸና ሓላፊነት ያልተሰጣቸው ሌላ አካላት ጣልቃ ገብተው ተጽዕኖ እንዲፈጥሩ እድል ስለሚሰጥ ዘወትር አስፈላጊ የሆኑ ጥንቃቄዎች ሁሉ መደረግ እንዳለባቸው እናምናለን፡፡

የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደር ጉባኤም በቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠው የማስፈጸም ሥልጣን የተወሰኑትን ደንቦች፣ መመሪያዎችና ልዩ ልዩ ውሳኔዎች ተግባራዊ ማድረግ፤ ከእያንዳንዱ የሥራ ዘርፍ በሚቀርበው ጉዳይ ላይ እየተወያየና የሥራ አፈጻጸም ስልት እያወጣ መወሰን፤ በሚመለከተው ደረጃ የአስተዳደር ችግሮች ሲፈጠሩ እያጠና መፈትሔ መስጠት፤ ከየሀገረ ስብከቱ በይግባኝ የሚመጡ ጉዳዮችን መወሰን እንደሆነ ይታወቃል፡፡ እነዚህ ተግባራት ሁሉ ግን የቅዱስ ሲኖደስን ሥልጣን ከማክበር ጋር፤ ለወሰናቸውም ውሳኔዎች ከመገዛት ጋር የሚፈጸሙ ናቸው፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን በቅዱስ ሲኖደስ ውሳኔ ላይ ተጽዕኖ የመፍጠርና አግባብ ያልሆነ የውሳኔ አተረጓጐምን የመከተል አካሔድ እንዳይኖር ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለበት እናምናለን፡፡

በአጠቃላይ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ በቤተ ክህነቱ አሠራር ውስጥ ይመለከተናል የሚሉ ወገኖች ሁሉ ቅዱስ ሲኖዶስ ያለውን የሕግ አውጪነትና ተርጓሚነት ሥልጣን አምኖ መንቀሳቀስ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ተቋማዊ አሠራር ሕልውና የግድ የሚያስፈልግ ነው፡፡ በመሆኑም እነዚሁ አካላት ለቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች ተግባራዊነት እንዲተባበሩና በውሳኔዎቹ ይዘቶች ላይ ያሉ ብዥታዎችንም ራሱ ቅዱስ ሲኖዶስ ግልጽ የሚያደርግበትን የራሱን አሠራር መጠበቅና ማስጠበቅ ይገባቸዋል፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔን እየተሰበሰቡ በመቃወም ሥልጣንና ቅድስናውን የመፈታተን አካሔድ ከወዲሁ ሊገታ ይገባዋል፡፡

በሃይማኖት ተቆርቋሪነት ስም የብፁዓን አባቶችን ስም በማጉደፍ፣ ለማጉደፍም በመዛት በአባቶች መካከል መለያየትን የሚያሰፍኑ በሥልጣንም ሆነ በሓላፊነት የማይመለከታቸው ግለሰቦችም ሆኑ ቡድኖች ከድርጊቶቻቸው መቆጠብ ይኖርባቸዋል፡፡ እንዲህ ያሉ ወገኖች ከምንም በላይ ለቤተ ክርስቲያን ሰላምና አንድነት የማይጨነቁ ከሆነ፣ በመንፈስ ቅዱስ ለተሾሙ አባቶችም ክብርን የመስጠት ፍላጐት ካጡ፣ እንዲሁም አባቶች በቅዱስ ሲኖዶስ በሚኖራቸው የመወሰን ድርሻ ላይ ተጽእኖ የመፍጠር አዝማሚያ ማሳየታቸውን ከቀጠሉ ማኅበራችን ድርጊታቸውን ከማውገዝ ባለፈ በሃይማኖት ወገንተኝነታቸው ላይ ጥያቄ ይኖረዋል፡፡

በሌላም በኩል አንዳንድ የግል መገናኛ ብዙኃን በሚያቀርቡት የተዛባ መረጃ ጉዳይ በሚመለከታቸው የቤተ ክህነቱ ወገኖች ላይ ስጋትና ጥርጣሬ ከመፍጠር አልፎ ከፍተኛ ችግሮች እያስከተለ ነው፡፡ ይህ አካሔድ ለኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ዕድገትና ጥንካሬ ለዓመታት ሲንቀሳቀስ የቆየውን ማኅበራችንን ማኅበረ ቅዱሳንን በእጅጉ ያሳስበዋል፡፡ በመሆኑም እነዚህ የመገናኛ ብዙኀን በእውነተኛ ምንጮች ላይ ተደግፈው እውነተኛ መረጃዎችን በመስጠት ችግሩን ለመፍታት እንዲንቀሳቀሱ መጠየቅ እንወዳለን፡፡

ካህናትና ምእመናንም ቤተ ክርስቲያናችን ከእግዚአብሔር ጋር የምንገናኝባት የክርስቶስ ሙሽራ መሆኗ ተጠብቆ እንዲቀጥል የፈጣሪም ረድኤትና በረከት እንዳይለየን ለሰላሟና አንድነቷ በንቃት መቆም ይገባናል፡፡ ምእመናን ዓሥራት በኩራት አውጥተው የሚያስተዳድሯት ቤተ ክርስቲያን በመሆኗ የቅዱስ ሲኖዶስ ሰማያዊና ሉዓላዊ ሥልጣንን በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ መሠረት የማስከበር የማይተካ ሚና አላቸውና፡፡ በመሆኑም ምእመናን ጉዳዮችን የራሳችን ጉዳይ በማድረግ ቤተ ክርስቲያን በየጊዜው ከሚያጋጥማት ፈተና እንድትድን በጾም በጸሎት እንድንበረታ መልእክታችን ነው፡፡

ምእመናንን ዕለት ዕለት በማገልገል ከምድር የሆነውን ብቻ ሳይሆን ሰማያዊውን ደመወዝ በተስፋ የሚጠባበቁ ካህናትም በጾም በጸሎት ከመትጋት ባሻገር በፈተና ጊዜ ፈተናን ለማስረግ አጋጣሚዎችን የሚጠቀሙ የቤተ ክርስቲያንን ጠላቶች መከታተልና ማስታገስ ይጠበቅባቸዋል፡፡

ከምንም በላይ ደግሞ በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ ምዕራፍ ሁለት አንቀጽ ስድስት እንደተቀመጠው የክርስቲያን ወጣቶች እንቅስቃሴ እንዲጐለብት ቅዱስ ሲኖዶስ ዓላማው አድርጐ እየሠራ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በመሆኑም በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መመሪያ ሥር ሆነን አገልግሎት እየሰጠን ያለን ሰንበት ት/ቤቶችና ማኅበራት የቅዱስ ሲኖዶስን ሰማያዊና ሉዓላዊ ሥልጣን ማስከበር ለሥራችን ስኬትና ለምናገለግላት ቤተ ክርስቲያን ተቋማዊ ጥንካሬ ወሳኝ መሆኑን ልንረዳ ይገባል፡፡ ስለዚህም በተለያዩ ጊዜያት ቤተ ክርስቲያናችን ከውስጥና ከውጪ የሚገጥማትን ፈተና ለመቋቋም ጥረት ማድረግ ይገባናል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም ይህን ድርሻውን ተረድቶ የሚንቀሳቀስ መሆኑን እየገለጸ፤ በቀጣይም በቅዱስ ሲኖዶስ የሥልጣን የበላይነት በቤተ ክርስቲያናችን አንድነት እና በቅዱስ ¬ትርያርካችን አባትነት ላይ የጸና አቋም እንዳለው በግልጽ ማስቀመጥ ይፈልጋል፡፡ ለዚህም እውን መሆን ከሚተጉ አካላት በመተባበር ያላሠለሰ ጥረት ማድረጉን እንደሚቀጥል መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡

                                                            ወስብሐት ለእግዚአብሔር።

የተዘጉ በሮች ይከፈቱ

ብዙዎቻችን ከእኛ ውጭ ስላሉ አካላት ሲነገረን ለማድመጥ የምንፈልገው የሆኑትንና እውነታውን ሳይሆን እኛ ሊሆኑት የምንፈልገውን ነው፡፡ ስለዚህም ስለምንነቅፋቸው አካላት የሚከሰሱበትንና የሚጐነተሉበትን እንጂ እውነታውን መስማት አሁን አሁን የኮሶ ያህል የሚሰቀጥጥ፣ የሞትም ያህል የሚያስደነግጥ ሆኖአል፡፡ እንዲህ ያሉት ነገሮች የሚከሰቱት ደግሞ በሁሉም ማኅበረሰብ መሆኑ ነገሩን የበለጠ አሳሳቢ ያደርገዋል፡፡
ፖለቲከኞች፣ የማኅበረሰብ መሪዎች፣ ምሁራን፣ የሃይማኖት ሰባክያንና መዘምራን፣ … እንዲሁም ሌሎችም ከዚህ ወጥመድ ሊያመልጡ አልቻሉም፡፡ ለምሳሌ ያህል የእስልምና መምህራኑ ስለ ክርስትና የሚሰሙት ክርስቲያኖች የሚሉትን ሳይሆን የአሉባልታ ዶክመንቶች የሚሉትን መሆኑ ሊጠቀስ ይችላል፡፡ የሃይማኖት ልዩነት በሌለበት እንኳ አንዱ ስለሌላው የሚናገረውና ሊሰማ የሚፈልገው አሁን አሁን አስፈሪነት እየታየበት ነው፡፡
 
ችግሩ የሐሳብ፣ የአመለካከት፣ የሃይማኖት፣ የርእዮተ ዓለም ልዩነት መኖሩ አይደለም፡፡ አንዱ የሌላውን በትክክል ተረድቶ ተጠየቃዊ በሆነ መንገድ የሐሳብ ክርክር መኖሩም ችግር ሊሆን አይችልም፡፡ እንዲያውም ጤናማ በሆነ አመለካከትና መረጃዎችን በመተንተን ላይ የተመሠረተ ከሆነ ልዩነትን አንጥሮ ለማወቅ ብቻ ሳይሆን በሐሳብ ለመሳሳብና ለመቀራረብም ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል፡፡ በሃይማኖትም ቢሆን አንዱ ሌላውን ሳይሰድብ የሚያምነውን በትክክል ተረድቶ ያንን እምነት እንዴት ስሕተት እንደሆነ ማሳየትም የሚጠበቅና ጤናማ ጠባይ ነው፡፡ ችግሩ ግን ሁሉም ስለሌላው የሚናገረው እምነቱን የሚመራበትን መጽሐፍ ለራሱ አሳብ አስረጂ አድርጎ በማቅረብ ብቻ ነው፡፡ ሊሆን የሚገባው ግን መጽሐፉ የሚያስተላልፈውን ትርጉም በአማኞቹ ዘንድ ያለውንም በመረዳት ጭምር ቢሆን ነበር፡፡
 
ከዚህም አልፎ በአንድ ተቋም ሥር ያሉ አስፈጻሚዎች እርስ በርሳቸው በተለያዩ የሐሳብ ማዕዘናት ላይ ተቀምጠዋል፡፡ አንዱ ሌላውን በጐሪጥ ከማየት አልፎ ለሚሠራው ሥራ ሁሉ የሚሰጠው ትንታኔ አንድን ዘውግ መሠረት ያደረገ ይሆናል፡፡ ሌላው ደግሞ ያን ሸሽቼ አመልጠዋለሁ በማለት ሌላ ጽንፍ ውስጥይወድቃል፡፡ … መንገዱ ሁሉ የዳጥና የመሰናክል፤ የተዛባ ትርጓሜና ጽንፈ ኝነትና ጎጠኝነት የበረዙት ሆኖአል፡፡
 
እነዚህን ችግሮች የማይቀበልም ያለ አይመልስም፡፡ ፖለቲከኞችም፣ የሃይማኖት ሰዎችም፤ ሌሎች ማኅበራትና ተቋማትም ችግሮቻችን ከእነዚህ የሚመነጩ እንደሆኑ ይስማማሉ፡፡ ሁሉም በሁሉም ላይ ሐሳብ ይሰጣል፡፡ ሌሎችን ችግሩ ውስጥ አሉ ይላል፤ ራሱ ግን ነጻ ነው፡፡ ሌሎች ከችግራቸው እንዲወጡ ሐሳብ ያቀርባል፤ ርእዮቱን፣ ትንታኔውንም ያቀርባል፤ ከዚህም አልፎ ስለሀገሩም ሆነ ስለሌላው ሐሳብ ሲሰጥ በሐዘንና በቁጭት ነው፡፡ እጅግ የሚያዝነውም ሌሎቹ የእርሱን ሐሳብ ለመስማት ባለመዘጋጀታቸው ነው፡፡ እርሱ ራሱም ግን በሌሎቹ እንዲህ እንደ ሚታዘንበት ትንሽ እንኳ ግምትና ጥርጣሬ የለውም፡፡ ሌሎች እርሱን በተሳሳተ መንገድ እንደሚረዱትና የትንታኔያቸውም ስሕተት ከዚህ እንደሚመነጭ ይጠቅሳል፡፡ የእርሱ ትንታኔ እንደዚህ ዓይነት ችግር ሊኖርበት እንደሚችል ግን አይገምትም፤ ቢነገሩትም አይሰማም፤ ቢሰማም አያዳምጥም፤ ቢያዳምጥም አይቀበልም፡፡ በሐሳብና በአመለካከት ወጪ እንጂ ገቢ የለውም፡፡
 
የዚህ ሁሉ ችግሩ ምንድን ነው? መደማመጥስ እንዴት ጠፋ? መመለሻውስ ምን ይሆን) … ብዙ ጥያቄዎችን እንድናነሣ እንገደዳለን፡፡ ችግሩ አንድና አንድ ነው፡፡ በየሰው ልቡና የተዘጉ በሮች አሉ፡፡ እነዚያ መከፈት ይገባቸዋል፡፡ ካለበለዚያ ደረቅ ጩኸትና ከንቱ ድካም ይሆናል፡፡
 
አይሁድ ጌታን /የስም አጠራሩ ከፍ ከፍ ይበልና/ አንዴ የዮሴፍ ልጅ ነው፣ ሌላ ጊዜ ደግሞ ጋኔን ያደረበት ነው፤ ሌላ ጊዜ በዓል ይሽራል፤ … እያሉ በእርሱ አምነው ከመጠቀም የተከለ ከሉት ሊሰሙት የሚፈልጉት ይህንኑ ብቻ በመሆኑና እውነቱን ለማድመጥ ደግሞ የልባቸው በር ስለተዘጋ ነበር፡፡ መዘጋቱን የማይቀበሉት ደግሞ ለእግዚአብሔራቸው የበለጠ የቀኑ ስለሚመስላቸው ነበር፡፡ ይህን በመንፈስ ቅዱስ የተመለከተው ቅዱስ ዳዊት «መኳንንት ደጆቻችሁን ክፈቱ፣ የክብር ንጉሥ ይግባ» ሲል ተናግሮአል፡፡ መዝ.23-2  በርግጥም የብዙዎቻችን ችግር ይህ ነው፡፡ እንደተጻፈውም እውነት የሆነው ጌታ ብቻ ነው፡፡ ያለ እውነት እርሱን ልናገኝም፤ ያለእርሱም እውነተኞች ልንሆን አንችልም፡፡ እርሱን ለመቀበል፤ እውነቱንም ለመረዳት ግን የልቡናችን በር ተዘግቷል፤ ተቆልፎአልም፡፡
 
ጌታ ለዮሐንስ ወንጌላዊ እንደገለጸው «በደጅህ ቁሜ አንኳኳለሁ፤ ለሚከፍትልኝ ሁሉ ወደ እርሱ እገባለሁ …» ብሎናል፡፡ ራዕ3-20 በርግጥም አሁን እግዚአብሔር የትው ልዱን የተቆለፈ ደጅ እየመታ ነው፡፡ መገናኛ ብዙኅኑም፣ ቃለ እግዚአብሔርም፣ ሌላውም ሁሉ ሳያውቁትም ቢሆን እንደነ ሊቀ ካህናት ሀናና ቀያፋ እውነቱን የሚናገሩበት አጋጣሚ አልጠፋም፡፡ ነገር ግን ስለመቻቻል የሚሰብኩት ሲችሉ አይታዩም፤ ስለ እውነት የሚሰብኩትም እውነት መናገር ተስኖአቸዋል፡፡ ስለ ፍቅር የሚነግሩን በጥላቻ ሰክረዋል፤ ስለነጻነት የሚተርኩልንም በቂም አርግዘዋል፤ አፋቸው ተከፈተ እንጂ የልቡናቸው በር አሁንም እንደተዘጋ ነውና፡፡
 
ስለዚህ መፍትሔው የልቡናችን በር መክፈት ነው፡፡ በዘረኝነት፣ በጎሰኝነት፣ በዘውገኝነት፣ በጽንፈኝነት፣ በጥላቻና በመሳሰሉት የተዘጉት ሁሉ መከፈት አለባቸው፡፡ ይምረረንም፣ ይጣፍጠንም፣ እስኪ ልቡናችንን ከፍተን አእምሮአችንን ከጥመት፣ ከፍርሃትና ከጥርጣሬ አጽድተን እናዳምጥ፡፡ በርግጥስ እውነታው የቱ ነው) በትዕግሥትና በበጎ ኅሊና ካደመጥን ሌሎቹ እንኳ ተሳስተው ከሆነ ቢያንስ ስሕተታቸውን በትክክል ለመረዳት ያስችለናል፡፡ ይህ ደግሞ ስሕተታቸው የምንለውን ገልጦ ለማስረዳትና በሐሳብ ለመሳሳብ ወደ አንድነትም ለመምጣት ይረዳናል፡፡ ያ እንኳ ባይሆን ባልሆኑት እንዳንነቀፍ ለመጠበቅ ያስችለናል፡፡

በሀገር ላይ ለውጥ ይምጣ፣ መነቃቀፎችና መጠላላቶችም ባሉበት ይቁሙ የምንል ከሆነ የተዘጋ ልቡናችን መከፈት ይኖርበታል፡፡ በጊዜው ያልተከፈተ የተዘጋ ደጅ ደግሞ በኋላ ቢከፈት እንኳ እውነቱን ለመረዳት ያስቸግረናል፡፡ በመኃልየ መኃልይ ላይ እንደተገለጸው «እግሬን ታጥቤያለሁ እንዴት አቆሽሸዋለሁ? ልብሴን አውልቄያለሁ እንዴት እለብሰዋለሁ? ተኝቻለሁ እንዴት እነሣለሁ?…» እያልን ምክንያቶችን በመደርደር ደጃችንን ካልከፈትን የእውነት ጌታ ከእኛ ይሔዳል፡፡ ከዚህ በኋላ ደግሞ «ብንፈልገውም አናገኘውም»፡፡ መኃ.5-2-7 ከዚህም አልፎ የከተማው ጠባቂዎች የተባሉት ክፉዎች መናፍስት አግኝተው ይቀጠቅጡናል፡፡ ስለዚህም ወደባሰ የኅሊና ጉዳትና ቁስል እንሸጋገራለን፡፡ ያን ጊዜ «… ለማይረባ አእምሮ አሳልፎ ሰጣቸው» የተባለው ይፈጸምብናል፡፡ ሮሜ1-28 ይህ ሁሉ ከመሆኑ በፊት ጆሮአችን ይስማ፤ አእምሮአችን ያድምጥ፤ ልቡናችንም ያስተውል፤ ያን ጊዜ የተዘጋው በር ይከፈታል፤ የቆመውም ጌታ ወደ ልቡናችን ይገባና እንፈወሳለን፡፡ ስለዚህ ሁላችንም በተለያየ የፍልስፍና ቁልፎች የዘጋነውን የልባችን ደጆች እንክፈት፡፡ አርኅው ልኀተ መኳንንት ይባዕ ንጉሠ ስብሐት፤ መኳንንት ደጆቻችሁን ክፈቱ፤ የክብር ንጉሥ ይግባ፡፡ መዝ.23-7፡፡

 

የይሁዳ ሰላምታ የቀሪ ሒሳብ ማስተካከያ ነው

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይሁዳን ከሐዋርያት እንደ አንዱ የመረጠበት ምስጢር እጅግ ጥልቅ ነው፡፡ ይህን ባናውቅ፣ ታሪኩ ባይጻፍና መምህራኑም በየጊዜው ባይነግሩን ኖሮ ዛሬ ብዙዎቻችን እንጨነቅ እንታወክም ነበር፡፡ እርሱን እንድናስታውሰው ያደረገን ደግሞ «ሃይማኖተ አበው የኢትዮጵያ ተማሪዎች ማኅበር» ያቀረበው ተደጋጋሚ ጥያቄ ነበር፤ በቤተ ክርስቲያኒቱ ፈቃድ ተሰጥቶት የመንቀሳቀስ ጥያቄ፡፡ ጉዳዩን በቀጥታ ከማየታችን በፊት ግን ጌታችን ይሁዳን ሐዋርያ አድርጎ በመምረጡ ካስተማረን ትምህርት እንነሣ፡፡
በትውፊት እንደሚታወቀው ይሁዳ ሳያውቀውም ቢሆን አባቱን ገድሎ እናቱን አግብቶ ይኖርበት ከነበረው ሕይወት የመጣ ሰው ነው፡፡ ጌታችን ንስሐውን ተቀብሎ እርሱን ከሐዋርያት እናቱንም ከቅዱሳት አንስት ደመራቸው፡፡ ጌታ አምላክ ነውና የይሁዳን ምንነት ብቻ ሳይሆን ወደፊት ርሱንም እንደሚሸጠው እያወቀ ለምን ሐዋርያው አደረገው) ልንል እንችላለን፡፡ ቢያንስ የሚከተሉትን ነገሮች እንድንማር ነው፡፡

ጌታ ለሚመለሱት ሁሉ እውነተኛ መሐሪ ነው፡፡ በተመለ ሰበት ጊዜ ፈጽሞ ይቅር ብሎ ወደ ማኅበረ ሐዋርያት ማም ጣቱ ፍጹም ፍቅሩንና ለተልእኮ የሚመርጠውም ሰው ተነሳሒ መሆኑን ያሳየናል፡፡ ጌታችን ድንግላዊ ዮሐንስን ብቻ አልመረጠም፤ ይህ እንግዲህ የሐዲስ ኪዳኗ ቤተ ክርስቲያን እውነተኛ ተነሳሕያን ለቅድስና የሚያበቃ የጽድቅ በር መክ ፈቷን የሚያውጅ ነበር፡፡ በዚህም የጌታችንን ፍጹም ይቅር ታና የምርጫውን ፍጹምነት እንማርበታለን፡፡

ከዚሁ ጋር ተያይዞም ጌታችን ምንም አምላክ በመሆኑ የነገውን የይሁዳን ድርጊት ቢያውቅም ገና ባልበደለው በደል ግን ቀድሞ አልገፋውም፡፡ በዛሬ ማንነቱ ብቻ የተቀበለውን ሰው ክብሩንም ሓሳሩንም የሚወስነው ዛሬውኑ በሠራው ሥራ መሆኑን ለማስተማር ነው፡፡ የዚህ ተጨማሪ ጉዳይ ደግሞ ክፉን ሰው ምክንያት ማሳጣት የሚገባ መሆኑንም ለመናገር ነው፡፡
 
ይሁዳን በመዋዕለ ስብከቱ ከክብር ሳያሳንስ፣ መዓርግ በመስጠት ያኖረው በኋላ ሹመት አጉድሎብኝ ነው እንዳይ ለውም ጭምር ነበር፡፡ በዐሥራት ላይ ሾሞ፤ የገንዘብ ፍላጐቱንም እንደተመኘ ይወጣለት ዘንድ ነጻ ፈቃድን ሰጥቶ ስርቆቱን ታግሶታል፡፡ ጌታ ዐሥራቱን በሌላ ሐዋርያ እጅ ቢያደርገው እንዲጠበቅ እያወቀ ለይሁዳ የሰጠው ጾሩ ቢቀልለት ብሎ ብቻ ሳይሆን ምክንያትም ሊያሳጣው ነውና፡፡ ይህም ከሆነ በኋላ ሲሰርቅ በፍጹም ታግሦታል፡፡ ስለዚህም ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ቤተ ክርስቲያን ዘክርስቶስ እንደ ይሁዳ ሙዳየ ምጽዋት የሚገለብጡትን እንደ ይሁዳ ታግሣቸው ትኖራለች፡፡ የይሁዳን የሌብነት ደረጃ ከፍተኛ መሆኑን ያየነው ደግሞ በጸሎተ ሐሙስ ዕለት ማታ እጁን ከወጭቱ መስደዱን ጌታ ገልጦ በመናገሩ ነው፡፡ «የለመደ ልማድ ከማድ ያሰርቃል» እንደሚሉት እንኳን ለሌላ ከመጣው ለራሱም ከተሰጠው የሚሰርቅ ምን ያህል ቢከፋ ይሆን) ዛሬም እንደ ይሁዳ ውሳጤ ውሳጢት /ቅድስተ ቅዱሳን/ ገብተው ለእነርሱ ብቻ የተፈቀ ደው ምስጢር ላይ እጃቸውን ያለአግባብ የሚጭኑኮ መጻሕፍቱንና ንዋያቱን የሚሰርቁ ሲያጋጥሙ ቤተ ክርስቲያን ብታዝንም የማትታወከው ነገሩን ቀድማ ከይሁዳ ሕይወት ስለ ተረዳችው ነው፡፡ ከላይ የጠቀስናቸውን ሁሉ ብዙ ጊዜ ሰምተናቸው ይሆናል፡፡ ችግሮቹም በየጊዜው የሚገጥሙን ስለሆነ አሁን አሁን አያስደንቁንም፡፡

ትልቁና ዋናው ጉዳይ ይልቁንም ለዛሬው ጉዳይችን የሚቀ ርበው ይሁዳ በመጨረሻው ሰዓት የፈጸመው ድርጊት ነው፡፡ ይሁዳ ተጠቃሚ ስለነበር ከሐዋርያት ጋር ጌታን እየተከተለ ይቆይ እንጂ ልቡ እንደ ጸሐፍት ፈሪሳውያን ነበር፡፡ ይህም የታወቀው ሠላሳ ብር የጐደለበት በመሰለውና ማንነቱ በተነገ ረው ጊዜ ወደ እነርሱ በማምራቱ ነበር፡፡ ጌታም ራሱ ይሁዳ ባለበት ስለይሁዳ የተናገረው በአካል ከሐዋርያት ጋር ቢሆንም በምግባርና በአመለካከት ከእነ ሀና እና ቀያፋ ጋር በመሆኑ ነበር፡፡ በይሁዳ ሕሊና ያለው ግን አሁንም ሌላ ብልጠት ነበር፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ ራሱን የተሻለ አሳቢ አድርጎ ስለወሰደ ከሐዋርያት ተደብቆ ከፈሪሳውያን ገንዘብ ተቀብሎ ጌታን አሳልፎ ከሰጠ በኋላ ጌታ በተአምራት ሲሰወርለት ገንዘቡንም አግኝቶ ከሐዋርያትም ጋር ሆኖ ለመኖር ነበር፡፡ ይህ ባልተሳካለት ጊዜ /ጌታ ራሱን አሳልፎ በሰጠ ጊዜ/ ደግሞ ፈጥኖ የታነቀው ሲኦል ገብቼ ካገኘኝም ትቶኝ አይወጣም ብሎ ጽድቁንም በብልጠትና በቀመር ሊፈጽም ነበር፡፡ ሁሉም ግን አልተሳካም፡፡ ድኅነትን በየዋሕነትና በእውነተኛ ንስሐ እንጂ በብልጠትና በቀመር ሊያገኙት አይቻልምና፡፡

ይሁዳ ከማርያም ባለሽቱዋ ቀረብኝ ያለውን ገንዘብ ለማግኘት የተጠቀመበት ስልት «ሰላምታ» ነበር፡፡ ነገሩን ከሊቃነ ካህናቱ ጋር ከጨረሰ በኋላ እርሱ «ሰላም» ብሎ ሊሰጥ በዚህም እነርሱ ጌታን ይይዛሉ፤ ለእርሱ ደግሞ እንደመሰለው በስውር ገንዘቡን ተቀብሎ ከጌታም ጋር ሊኖር ነበር፡፡ የዚህ ነገር ፍጻሜው ታላቅ ጥፋት መሆኑን ብናውቅም ነገር ግን ቤተ ክርስቲያን ይህን ስልት እየተጠቀሙ ደሟን የሚያፈስሱ ጠላቶቿ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ከቤተ ክርስቲያን እንደማይጠፉ እውነተኛውን ትምህ ርት ትቶልን አለፈ፡፡

በዕሥራ ምእቱ መጨረሻ በ«ሃይማኖተ አበው የኢትዮጵያ ተማሪዎች ማኅበር» ስም የሚወጡት የሚወርዱት «ውስጠ ዘ» ዎች ጥያቄም ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡ እንደ ይሁዳ ቤተ ክርስቲያን ነበሩ፤ እንደ እርሱ ኮረጆአቸውን ይዘው ከዓለም አቀፍ የፕሮቴስታንት ተቋማት የሚፈልጉትን ሰበሰቡ፡፡ ቤተ ክርስቲያን ግን እንደ ይሁዳ አቅርባ ሾመቻቸው፡፡ ከአንድም ሁለት ጊዜ ጥያቄያቸውን ተቀብላ ፈቃድ ሰጥታ ቢሮ ከፍታ ሰየመቻቸው፡፡ እነርሱ ግን ከግብራቸው አልተመለሱምና ማኅ በሩ በይፋ ተዘጋ፡፡ ደግነቱ ይሁዳ ገንዘቡን ለራሱ በተመኘ ጊዜ ሐዋርያትን ጨምሮ ለማሳመጽ «ይህ ሽቶ ተሽጦ ለድሆች ያልተሰጠ ለምንድን ነው?» በሚል ደስ በሚያሰኝ ቃል ቅስቀ ሳውን ቢያደርግም ከሐዋርያት የተከተለው አለመኖሩ ነው፡፡ ሃይማኖተ አበውም ከጥንቶቹ ቀናዕያንና ንጹሐን አባላቱ እር ሱን የተከተለው የለም፡፡ እነርሱ እንደ ሐዋርያት በታማኝነት አገልግሎታቸውን ቀጥለዋልና፡፡ ይሁን እንጂ በመካከለኛ ዕድሜ ከነበሩ ወጣት ዘማርያን መካከል ለሙሉ ወንጌል፣ ለሬማና ለመሳሰሉት የገበራቸው ወንድሞቻችንና እኅቶቻችን የሚዘነጉ አይደሉም፤ አሁንም የሚያሳዝኑን ሆነው ቀርተዋልና፡፡

ይህ ሁሉ ሳያንሰው አሁንም በተድበሰበሰ መንገድ እንደገና ፈቃድ ይሰጠኝ፤ ቢሮ ልክፈት የሚለው ጥያቄውን አቅርቧል፡፡ ይህ ጥያቄ ጥንት ማኅበሩን መሥርተው በቅን መንገድ ቤተ ክርስቲያንን አገልግለው፤ የማኅበሩ አመራር ማኅበሩን ወደ ተሳሳተ አቅጣጫ ሲወሰደውም እነርሱ በቤተ ክርስቲያናቸው ጸንተው ከቀጠሉትና አሁንም እያገለገሉ ካሉት እውተኛ ልጆቿ ቀርቦ ቢሆን ኖሮ ምን ያህል ያስደሰት ነበር፡፡ ስለዚህም እነዚህን አካላቱን ለስምና ለዝና ብቻ የሚፈልጋቸውና የተደበቀ ጅምር ዓላማውን /ፕሮቴስታንት የማድረግ ግቡን/ ይዞ ሲንቀሳ ቀስ የኖረው የማኅበሩ አመራር ግልጽ ባልሆነ ሁኔታ በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ በኩልና ራሱም አድበስብሶ ያለ ማንም ሰው ፊርማ ያቀረበው ጥያቄ ዝም ተብሎ የሚታለፍ አይደለም፡፡

ማእምረ ኅቡአት ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰወረውን ዓላማ የሚ ገልጥበት ጊዜው ሩቅ ባይሆንም እንዲህ ያለው ቀረቤታ ከይ ሁዳ ሰላምታ ተለይቶ የሚታይ ሊሆንም አይችልም፡፡ ይሁዳ ጌታችንን ሰላም ያለው በአይሁድ ለማስያዝና ቀረብኝ ያለውን ገንዘብ ለማግኘት እንደነበረው ሁሉ የዚህ ጥያቄ ዓላማም ያው ቀሪ ሒሳቤን ላወራርድ የማለት ይመስላል፡፡ ለእርሱ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችን የዚህን «ሰላምታ» ትርጉም ነገሮናል፤ መልእክቱንም አስተምሮናል፡፡ ምክንያቱም ጌታ ይሁዳን ንስሐም ሲገባ ያውቀዋል፤ ሊያታልለውም ሲመጣ ያውቀዋል፡፡ ይሁዳ አጥፍቶ ነው የወጣው፤ ስለዚህ ሲመለስ ንስሐ ይጠበቅበት ነበር፡፡ የእርሱ መልስ ግን ቀሪ ሒሳብ የማወራረድ ስለነበር ለንስሐ ፈቃደኛ አልነበረም፡፡ ስለዚህም በሰላምታው ሸንግሎ ቀሪ ሒሳቡን ለመውሰድ የመጨረሻ ዕድሉን ተጠቀመ፡፡

የ«ሃይማኖተ አበው» መሪዎችም እውነተኞች ቢሆኑ ኖሮ ማኅበር እንደመሆኑ መጠን ያጠፉትን ጥፋት ራሳቸው ዘርዝረው አቅርበው፤ ለዚያ የዳረጋቸውን ምክንያቱን ለይተው ቤተ ክርስቲያንን ለበደሉበት ይቅርታ ጠይቀው አጥፍተዋቸው ለቀሩት ልጆቿ እውነተኛ ንስሐ ገብተው ቢመለሱ እንዴት ባማረባቸው ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ ቢቻል ሌላ ሃይማኖት የገቡትን ለመመለስና ለንስሐ ለማብቃት ቢጥሩ በይፋ ስሕተታቸውን ገልጸው ጥፋታቸውን ነግረው ቢመለሱ ኑሮ አሁንም ያለው አገልግሎት እንኳን ለእነርሱ ሌላም ቢፈጠር የሚጋብዝ ነበር፡፡ ይህን ግን አላደረጉትም፡፡ ሊያደርጉት ሲጥሩም አይታዩም፡፡ ይልቁንም ውስጥ ለውስጥና በድብቅ እንደገና የጨለማ ሥራ፤ የይሁዳ ሸንጐ፡፡ ለሃይማኖተ አበው አመራርና ደጋፊዎቹም ሁልጊዜም ቤተ ክርስቲያን አልገባት /አልበራላት/ ብሎ እንጂ እነርሱማ አይሳሳቱማ፡፡ «እግዚአብሔር ሰማዩን ጠቅልሎ ሸሸ» እንዳለ ሰይጣን፤ «እኔ ወረድኩ» ማለትንማ አይሞክራትማ፡፡ እንዲህ ካለማ እውነት ሊወጣው ነው፡፡ አሁንም ግን ለትክክለኛው መንገድ ጊዜው አልመሸም፤ ልቡ ካለ፡፡
 
ካለበለዚያ ግን ጥያቄው ከይሁዳ ሰላምታ ፍጻሜውም ከእርሱ ፍጻሜ አያልፍም፡፡ ለዚህ ጉዳይ የቀድሞ እውነተኞቹ አባላት ዛሬም እንደ ጥንቱ ሓላፊነት አለባችሁ፡፡ በጎውን ዓላማ ማጥፋትና መንገዱን ማሳታቸው ሳያንሳቸው ጥፋታቸውን በስማችሁ ለማሳት መምጣታቸውን መግለጥ ያለባችሁ እናንተ ናችሁና፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን አባቶችም ጌታቸውን በመመሰል ይሁዳን እንደ አመጣጡ እንደሚመልሱት የታመነው ነው፡፡ ንስሐ ሲገባ ይቀበሉታል፤ አሳልፎ ሊሰጥ ሲመጣማ ጌታችን እንደጠየቀው «ለምን ነገር መጣህ)» ብለው ይጠይቁታል እንጂ ዝም አይሉትም፡፡ ስለዚህም ተጠየቅ፤ ለምን ነገር መጣህ) አብረውህስ ያሉት እነማን ናቸው? ሾተሉና ዱላውስ የማን ነው?