በእኛ ዘመን ምንጮቻችን እንዳይነጥፉ

ኅዳር  17 ቀን 2005 ዓ.ም.


የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዘርፈ ብዙ መንፈሳዊ አገልግሎት መሠረት የሆኑት፤ የአባቶች ካህናት፣ ሊቃውንት መምህራን፣ ጳጳሳት የአገልጋዮቿ መፍለቂያ፤ ለዘመናት የማይነጥፉ ምንጮች ሆነው የኖሩት አብነት ትምህርት ቤቶቻችን፤ በዚህ ዘመንና ትውልድ ህልውናቸውን ጥያቄ ውስጥ ያስገባ ፈተና እንደተጋረጠባቸው የዐደባባይ ምስጢር ከሆነ ቆይቷል፡፡

 

ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ የሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን አካላት እንዲሁም ቅን አሳቢ እውነተኛ ልጆቿ ሁሉ ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥተው የተግባራዊ መፍትሔው አካል በመሆን ሲንቀሳቀሱም ይታያል፡፡

 

እንዲህም ሆኖ ግን ከጊዜ ወደ ጊዜ ችግሩ እየተደራረበ መጥቶ በወቅቱ መሠረታዊ ለውጥና የተሻለ እድገት የሚያስገኝ መፍትሔ ባለመሰጠቱ የአብነት ትምህርት ቤቶቻችን ፈተና ከፍቷል /ተባብሷል/፡፡

 

የትምህርት አሰጣጥ ሥርዓቱ ጊዜና አካባቢያዊ ሁኔታዎችን ከመንፈሳዊና ቁሳዊ ሀብቶች ጋር በማገናዘብ ዘመኑን የዋጀ እንዲሆን አለመደረጉ፤ በተቀላጠፈና ወጥ በሆነ መንገድ ተደራጅቶ አለመሰጠቱ፤ የአብነት ትምህርት ቤቶች አደረጃጀት የመማሪያ ክፍሎች፣ የትምህርቱ መርጃ መሣሪያዎች፣ መጻሕፍት ወዘተ በፍጹም አለመሟላታቸው፤ የሊቃውንት መምህራኑ የኑሮ ችግርና በቂ መተዳደሪያ ድጋፍ አለማግኘት፤ የደቀ መዛሙርቱ ለረኃብና ለዕርዛት መዳረግ፤ መጠለያ ማጣት፤ የጤና ክብካቤና ትምህርት የሚያገኙበትና በዝቅተኛ ደረጃም ቢሆን የሕክምና አገልግሎት አለመኖር፤ በአንጻሩ ደግሞ ይህንን ሁሉ ችግርና መከራ ተቋቁመው ለዓመታት ደክመው ከሊቃውንት መምህራን አባቶቻቸው የዕውቀት ማዕድ የቀሰሙትን ዕውቀትና ሙያ ለቤተ ክርስቱያኒቱ አገልግሎት የሚያውሉበት የሥራ ዋስትና ማጣታቸው ከሌሎችም ውጫዊ ተግዳሮቶች ጋር ሲደመር ለመማር ማስተማሩ ትልቅ ፈተና ስለሆነ ወዘተ…. አፋጣኝ ተግባራዊ መፍትሔ የሚፈልግ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ሕልውናና ቀጣይነት ላይ የተደቀነ ገሐድ አደጋም ስጋትም ነው፡፡

 

ሁለንተናዊ ፈተናዎቹን በሚፈታ መልኩ መሠረታዊ መፍትሔ በአፋጣኝ ባይታይም፤ ይህንን ችግር በመቅረፍ የአብነት ትምህርት ቤቶቻችንን ከተደቀነባቸው አደጋ ለመታደግ ተስፋ ሰጪ ጥረቶች እየተደረጉ እንደሆነ ይታወቃል፡፡

 

ባለፈው የጥቅምት ወር 2005 ዓ.ም በተካሄደው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ፤ የአብነት ትምህርት ቤቶችን ለማጠናከር የተወሰነው የዐሥር ሚሊዮን ብር በጀት ለችግሩ የተሰጠውን ትኩረት የሚያመለክት፤ ለአስተማማኝ ቀጣይነቱም የተስፋ ብርሃን የሚፈነጥቅ ነው፡፡

 

ይህንን በድርሻው ለማጠናከር በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አማካኝነት፤ “የጥንቱ ከሐዲሱ ጋር በደጃችሁ አለ” በሚል መሪ ቃል ኅዳር 2 ቀን 2005 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ይፋ የሆነው፤ “አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የነጻ ትምህርትና ሥልጠና ዕድል” የአብነት ትምህርቱን ዘመኑን በዋጀ መልኩ በትውልዱ ቀጣይነት እንዲኖረው የሚያስችል መርሐ ግብር ነው፡፡

 

እንዲህ ዓይነቶቹ ተጠቃሽ የመፍትሔ እርምጃዎች ለቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ቀጣይነት ዋስትና ሰጪ ጥረቶች ናቸው፡፡ አፈጻጸማቸውን በተመለከተም የተቀናጀ አሠራር፤ የቅርብ ክትትልና ቁርጠኛ አገልግሎት ይፈልጋሉ፡፡ ችግሩ እየከፋ ከመምጣቱ አኳያም ቀዳሚ ትኩረትና አፋጣኝ የተግባር ክንውን እንደሚያስፈልግ የታወቀ ነው፡፡

 

አብነት ትምህርት ቤቶች ወቅቱና ትውልዱን እንዲሁም አካባቢያዊ ሁኔታዎችን በማገናዘብ ከዘመናዊው ትምህርት ጋር ተቀናጅተው የሚያድጉበትና የሚቀጥሉበትን መፍትሔ መፈለግና በተግባር ማረጋገጥ ለነገ የሚባል ጉዳይ አይደለም፡፡

 

በተለይም በገጠሩ አካባቢ የሕዝቡ የኑሮ ሁኔታና ለአብነት ትምህርቱ ያለው አመለከካከት እየተለወጠ መምጣቱን ተከትሎ ለመምህራኑና ለተማሪዎቹ የሚያደርገው ድጋፍ መቅረት ዐቢይ ችግር ነው፡፡ ይህንን ችግር ተረድቶ መፍትሔ የሚሆኑ ተተኪ አሠራሮችን መቀየስና በአፋጣኝ ተግባራዊ ማድረግ የግድ ይላል፡፡ ደቀመዛሙርቱ የነገይቷን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መስፋፋት ተስፋ አድርገው፤ ለዓመታት በችግርና መከራ ውስጥ እያለፉ በአብነት ትምህርቱ የቀሰሙትን ዕውቀትና ሙያ ይዘው ከተመረቁ በኋላ፤ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ተመድበው መተዳደሪያ አግኝተው ቤተ ክርስቲያንንም የሚያገለግሉበት አስተማማኝ የሥራ ዋስትና ሊሰጣቸው ይገባል፡፡ ዓለም አቀፋዊውንና አካባቢያዊ ሁኔታዎችን የሚገነዘቡበት፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ አጠቃላይ ለውጦችን በማስተዋል በቀላሉ ተረድተው የሚያዘጋጁበትና በነገ አገልግሎታቸው የትውልድ መሪ የምእመናን አለኝታ ሆነው እንዲቀጥሉ የሚያስችሏቸውን ተጨማሪ ትምህርቶች የሚያገኙበትን መንገድ ማመቻቸትና ተግባራዊ ማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡

 

የአብነት ት/ቤቶች ባልተስፋፉባቸው አህጉረ ስብከት የገጠርና ጠረፋማ አካባቢዎችም፤ የወቅቱን ተጨባጭ ሁኔታ ያገናዘቡና በሚገባ የተደራጁ የአብነት ትምህርት ቤቶችን ማቋቋም ያስፈልጋል፡፡ በየአካባቢው ቋንቋ ሊያስተምሩና ሊያገለግሉ የሚችሉ መምህራነ ወንጌልና አገልጋይ ካህናትን ማውጣት (ማፍራት) ቅድሚያ ከሚሰጣቸው ተግባራት አንዱ ነው፡፡

 

አለበለዚያ አገልጋይ ካህናትና መምህራነ ወንጌል በማጣት ከዕለት ወደ ዕለት የሚዘጉት በየገጠሩና በየበረሐው እንዲሁም በየጠረፉ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ቁጥር በከፍተኛ ፍጥነት እየጨመረ መምጣቱ አይቀርም፡፡ ከቤተ ክርስቲያን እቅፍ እየወጡ በሌሎች የሚነጠቁት ምእመናንም ቁጥር የዚያኑ ያህል እየጨመረ እነሱን ለመታደግ አስቸጋሪ ይሆናል፡፡

 

ተተኪ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እያነሱ፣ በየገዳማቱ የሚያገለግሉ እውነተኛ መነኰሳት እየቀነሱ፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም በሁለንተናዊ መንፈሳዊ አገልግሎቷ እየተዳከመች፤ በማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፍ የሚኖራት ተሳትፎ እየጠበበ፤ እስተዳደራዊ መዋቅሯና አሠራሯ ብቃት እያነሰው፤ ምእመናኗም በመንፈሳዊ ሕይወታቸው፣ በዕለት ተዕለት ኑሮአቸውና ማኅበራዊ ግንኙነታቸው የሚያበረታቸው፣ የሚመክራቸው፣ የሚከታተላቸው፣ የሚያጸናቸውና የሚያመላክታቸው እያጡ በዘመኑ ሥልጣኔ የባሕል ወረርሽኝ እየተዋጡ፣ ለማንነት ጥያቄያቸው ምላሽ እያጡ፣ ለሃይማኖታዊና ማኅበራዊ ቀውስ እየተዳረጉ ይመጣሉ፡፡ የዚህ ሁሉ ድምር ውጤት የሚያስከትለውን የከፋ ችግር ከወዲሁ ለመገንዘብ ከሁላችንም የሚሰወር እንዳል ሆነ ይታወቃል፡፡

 

ስለዚህ ዘርፈ ብዙ ለሆነው የቅድስት ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ አገልግሎት መሠረት የሆኑት፤ የሊቃውንቱ፣ የጳጳሳቱ፣ የአገልጋይ ካህናቱ፣ የመምህ ራነ ወንጌሉ ሁሉ መፍለቂያ ምንጮች አብነት ትምህርት ቤቶቻችን በእኛ ዘመንና ትውልድ ሳይነጥፉ እንዲቀጥሉ በተጠናና ችግር ፈቺ በሆነ መንገድ ጥረት የሚያደርጉትን አካላት በሚቻለን ሁሉ በማገዝ ከሁላችንም ተጨባጭነት ያለው ተሳትፎ ይጠበቅብናል፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በጎቿን ይዛ እንድትዘልቅ …

ጥቅምት 26 ቀን 2005 ዓ.ም.


በየዓመቱ በጥምቀት ወር በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የአስተዳደርና ዘርፈ ብዙ አገልግሎት ላይ የሚመክረው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ለሠላሳ አንደኛ ጊዜ ተካሂዷል፡፡ በዚህ ጉባኤ ላይ የእናት ቤተ ክርስቲያናቸውን የአገልግሎት ጥሪ የተቀበሉ ምሁራን ልጆቿ፤ በልዩ ልዩ ርእሰ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ ጥናት ጽሑፎቻቸውን አቅርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ በእንደዚህ ዓይነቱ ታላቅ ጉባኤ ላይ፤ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሁለንታዊ አገልግሎት መቃናት የሚበጁ፣ በየሙያ ዘርፉ ዕውቀትና ልምድ ባካበቱ ምሁራን ልጆቿ የሚቀርቡ የጥናት ጽሑፎችና የሚካሄዱ ውይይቶች፤ እናት ቤተ ክርስቲያን ትውልዱን ይዛ ዘመኑን እየዋጀች ጸንታ እንድትቀጥል በማድረግ ረገድ ጠቀሜታቸው የጎላ ነው፡፡

 

በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የአገልግሎት ዘርፎች የተቀላጠፈና ዘመናዊ የአስተዳደር መዋቅርና አሠራር እንዲኖር ማድረግ ወቅቱም ሆነ ትውልዱ የሚጠይቀው ጉዳይ ነው፡፡ በዕቅድ ላይ የተመሠረተ በሪፖርትና ትክክለኛ ክትትል ባልተለየው ግምገማ የተደገፈ፣ ሓላፊነትና ተጠያቂነት ያለበት ማእከላዊ የፋይናንስ አስተዳ ደር ሥርዐት እንዲሰፍን ተጨባጭ ጥረት ያስፈልጋል፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቷ መንፈሳዊ ፍርድ ቤቷ ተጠናክሮ አስተዳደሯ፣ ሥርዐተ ከህነቷም ሆነ ሁለንተናዊ አገልግሎቷን የሚመለከቱ እንዲሁም የምእመናን መንፈሳዊ ጉዳ ዮች የሚዳኙበት አስተምህሮና ቀኖናዋን የጠበቀ መንፈሳዊ የፍትሕ ሥርዓት ተግባራዊ እንዲሆን ማድረግ ችላ የሚባልበት ወቅት አይደለም፡፡

 

ከሐዋርያዊ ተልእኮዋ ባሻገር በማኅበራዊ አገልግሎቷም የበለጠ እንድትሠራ፤ በልማት ሥራ እንድትበለጽግ፣ ገዳማቷና አድባራቷ በገቢ ራሳቸውን ችለው ከልመና እንዲላቀቁ በማድረግ ረገድ ከፍተኛ ሥራ ይጠበቅባታል፡፡ በእነዚህ ሁሉ መስኮች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ምሁራን ልጆቿን በማሳተፍ በጥናትና ምርምር የተደገፈ ውጤታማ ሥራ ለመሥራት ቀዳሚ ትኩረት መስጠት እንዲሁም ሁኔታዎችን ማመቻቸትና የበለጠ ጥረት ማድረግ አለባት፡፡

 

አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ያለው ታላቅ መድረክ፤ በተራዘመ ሪፖርትና በተደጋገመ መልእክት የሚባክነው ጊዜ፤ በዓመት አንድ ጊዜ ከሚገኘው ጉባኤ ለቤተ ክርስቲያን የሚበጅ አሳብ፣ ዕቅድና መፍትሔ የሚቀርብበትን ምቹ ሁኔታ በማሳጣት ያለጥቅም እንዲያልፍ ያደርጋል፡፡ ለተሻለ አሠራርና ለበለጠ ውጤት የሚያበቃ የውይይት መድረክ የሚሆንበትን ዕድል ይነፍጋል፡፡

 

ስለዚህ እንዲህ ዓይነቶቹን ክፍተቶች በመገንዘብ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሁለን ተናዊ አገልግሎት የሚበጅ የጥናት ጽሑ ፎች እንዲቀርቡ ሐሳብ በመስጠት፣ ዕቅድ በማውጣት፣ ጊዜ፣ በጀትና የሰው ኀይል መድቦ ውይይቱ እንዲካሄድ የተደረገው ጥረትና የተከናወነው ሥራ የሚመሰገን ሲሆን ወደፊትም በተሻለ ሁኔታ ሊቀጥል የሚገባው ተግባር ነው፡፡

 

የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ጥሪ ተቀብለው እውቀታቸውንና ሙያዊ ልምዳቸውን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በሚበጅ ተግባር ላይ ለማበርከት በቀናነት የተሳተፉት ምሁራን ልጆቿ የሚመሰገኑ ናቸው፡፡ አገልግሎታቸው ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልእኮ መቃናት፣ በዘመናዊ አሠራር በተደራጀ አስተዳደራዊ መዋቅር ዘርፈ ብዙ አገልግሎቷ የተሳካ አፈጻጸም እንዲኖረውና በልማት እንድትበለጽግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረክታል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ አገልግሎት በልዩ ልዩ የሥራ መስኮችና ቦታዎች የተሰማሩት ምሁራን ልጆቿ በየተሰጣቸው ጸጋና ሞያ ለቤተ ክርስቲያን የሚጠበቅባቸውን አገልግሎት እንዲያበረክቱ በማነሣሣት ረገድ በአርአያነት የሚጠቀስ ነው፡፡

 

በየደረጃው ያሉት የቤተ ክህነቱ መዋቅርና አካላት ይህንኑ በጎ ልምድ መነሻ በማድረግ፤ በተለያየ ሙያና የሥራ መስክ የተሰማሩ ምሁራን በቤተ ክርስቲያን ልጅነታቸው ድርሻቸውን እንዲያበረክቱ በራቸውን ክፍት ማድረግና የአገልግሎት መድረኮችን ማመቻቸት እንደሚጠበቅባቸው ያመላክታል፡፡

 

በሠላሳ አንደኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ላይ ከቀረቡት ጽሑፎች መካከል፤ ለምሳሌ “የዘመናችንን ትወልድ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ለማብቃት የአባቶች ሚና” በሚል ርእስ የቀረበው ጽሑፍም ከላይ ያነሣና ቸውን ነጥቦች በአጽንዖት የጠቆመ ነው፡፡

 

በጥናት ወረቀቱ እንደተጠቀሰው፤ የሕዝብ ብዛት እየጨመረ በመምጣቱ ምክንያት ጎልቶ አይታይ ይሆናል እንጂ በየጊዜው ሃይማኖታቸውን የሚተው፣ ከቤተ ክርስቲያናቸው የሚኮበልሉ ምእመናን ቁጥር ቀላል አይደለም፡፡ ምእመናንን ወደ ውጪ የሚገፉ በርካታ ውስጣዊና ውጫዊ ምክንያቶች አሉ፡፡ ከእነዚህም ምክንያቶች አንዱና ዋነኛው ከቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ጋር የሚያያዝ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎቶች ይበልጥ እየተሻሻሉ ዘመኑን መዋጀት ካልቻሉ ውጤቱ ያማረ አይሆንም፡፡ ለዚህም ነው የዛሬውን ትውልድ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ብቁ እንዲሆን ማድረግ ወሳኝ ጉዳይ የሚሆነው በማለት የቀረበው ሐሳብ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ነው፡፡

 

ምናልባትም በታላላቅ ከተሞች ባሉ ገዳማትና አድባራት የሚታየው እንቅስቃሴ፤ በወርና በዓመት የንግሥ ወይም ዐበይት በዓላት የሚታየው የሕዝበ ክርስቲያኑ ብዛትና ድምቀት በየገጠሩና በየበረሐው ያለውን አገልግሎት እንቅስቃሴና የምእመናኑን መጠን የሚያሳይ ነው የሚል የተሳሳተ ግምት ካለ፤ ገሐድ እውነቱ ከተሳሳተው ግምት የተለየ መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

 

ስለዚህ ትውልዱን በቤተ ክርስቲያን እቅፍ ሰብስቦ ለአገልግሎት በማብቃት የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ አገልግሎት ዘመኑን በዋጀ ውጤታማ አሠራር በተሳካ ሁኔታ ማፋጠን የወቅቱ ጥያቄ ነው፡፡ አሁን ባለው ዘመንና ትውልድ ደግሞ ሉላዊነትን (Globalization) መሠረትና ጉልበት ያደረገ ሥልጣኔ የተስፋፋበት፣ ዘመናዊነት የነገሠበት እንደመሆኑ፤ በዓለማችን የሚከሠቱ ተጨባጭ ሁኔታዎች በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ አሉታዊም ሆነ አዎንታዊ ተጽዕኖ አቸው እያየለ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሕልውናና አገልግሎት ፈተናዎች እየሆኑ ይታያል፡፡

 

ከዘመኑ የኑሮ ሁኔታ፣ የሥልጣኔ ውጤቶች፣ በተዛባ የዘመናዊነት ግንዛቤ የሚከሠቱት ዓለም አቀፋዊ ተጽዕኖዎች በተለይ በመንፈሳዊ ሕይወቱ የሚያሳድሩበትን ጫና እንዲቋቋም አድርጎ ለጥያቄዎቹ ምላሽ በመስጠት ትውልዱን ይዞ ለመቀጠል ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አፋጣኝ መፍትሔ ልትሰጠው የሚገባ ተግባር ነው፡፡

 

ስለዚህ በየአጥቢያው የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን ማስፋፋት፣ ጉባዔያትን ማጠናከር፤ ለሰንበት ትምህርት ቤቶች ልዩ ትኩረት ሰጥቶ በቅርበት ዕለት ዕለት መከታተል፣ መምህራነ ወንጌል መመደብ፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማሟላት፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን በማጠናከርና በማስፋፋት አገልግሎታቸውም በበለጠ ጥረት የተሻለ ውጤት እንዲኖረው በማድረግ ረገድ ከፍተኛ ሥራ ይጠበቃል፡፡

 

ከፍተኛ የመንፈሳዊ ትምህርት ተቋማቱን በተሟላ አደረጃጀትና ዘመናዊ አሠራር እያጠናከሩ ማስፋፋት እውነተኛ የቤተ ክርስቲያን ልጆች በቀና ዓላማ ገብተው በቂ ዕውቀት ቀስመው ለአገልግሎት እንዲዘጋጁ ያስችላቸዋል፡፡ ሌሎችም የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መንገዶችን የቴክኖሎጂውን እድገትና ዕድል በመጠቀም፤ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ በመላው ዓለም በየቦታው ላይ ለምእመናን፤ በመገናኛ ብዙኃን ቃለ እግዚአብሔርን ማድረስ የግድ ይላል፡፡

 

አብነት ትምህርት ቤቶቻችን በብዙ ችግሮች ተተብትበው መምህራኑም ሆኑ ደቀ መዛሙርቱ ፈተና ላይ ወድቀዋል፡፡ የትምህርት አሰጣጥ ዘዴው ጊዜን፣ ቁሳዊ ሃብትን፣ ወቅትንና ሌሎችም አካባቢያዊ ሁኔታዎችን ባገናዘበ ሁኔታ ተመቻችቶ ባለመካሄዱ በቀጣይነቱ ላይ የተጋረጠ ትልቅ ፈተና ነው፡፡ ችግሮቹን አዝሎ ያንዣበበው አደጋ ከቀጠለ የካህናትና ሊቃውንት አገልጋዮቿ ምንጭ እየተዳከመ የነገይቱ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ስኬትም አጠያያቂ መሆኑን ከወዲሁ ማሰብ፤ አፋጣኝ መፍትሔ መፈለግና በተግባር ማረጋገጥ አስፈላጊ ነው፡፡ ሊቃውንቱ እንዲያስተምሩ፣ የተካበተ ዕውቀታቸው ለምእመናን እንዲደርስ መርሐ ግብር ማዘጋጀት፣ መድረኮችን ማመቻቸትና እንዲሳተፉ ማድረግ ይገባል፡፡ ከዚህም በላይ ሰፊ የዕውቀት ሀብታቸው፣ ከመንፈሳዊው አገልግሎትና ሕይወታቸው ልምድ ጋር ለትውልድ እንዲተላለፍ ምእመናን እንዲጠቀሙበት ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንዲጽፉ ማበረታታት፣ የሚያስፈልጋቸውን ማገዝ ማሳሰብ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡

 

የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አባቶችና አገልጋዮች ትውልዱን ከማስተማር ጎን ለጎን የዕለት ተዕለት ክትትልና መንፈሳዊ ጥበቃ ማድረግ እንዳለባቸው ዋነኛ የአባትነት ሓላፊነታቸው እንደሆነ የታወቀ ነው፡፡ ከዚሁ ጋር በሕይወታቸው መልካም አርአያ በመሆን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መትጋትና ሃይማኖታዊ ሓላፊነታቸውን በሚገባ መወጣት አለባቸው፡፡

 

በአጠቃላይ በጎቹን በቃለ እግዚአብሔርና በመንፈሳዊ ሕይወት ጠብቆ በእናት ቤተ ክርስቲያን እቅፍ እንዲዘልቅ፤ በቀና መንፈስ በአገልግሎት እንዲሳተፍ ማስቻል፣ በፍቅርና በመልካም የአባትነት አርአያ መቅረብ፣ መከታተል ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ቀዳሚ ሥራ ነው እንላለን፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት ቁጥር 4 2005 ዓ.ም.

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ቢያደርገው የምንላቸው ነጥቦች

ጥቅምት 12 ቀን 2005 ዓ.ም.

 

ቅዱስ ሲኖዶስ ኤጲስ ቆጶሳት የያዘውን፣ የታወቀ ሕጋዊ መንበር፣ ታሪካዊና ሕጋዊ መሠረት እንዲኖረው ሆኖ የተደራጀውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምልዐተ ጉባኤ ነው፡፡ ይህ ምልዐተ ጉባኤ ለአንዲቷ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አንድነትና ልዕልና እጅግ አስፈላጊና አንድ ነው፡፡

 

አስፈላጊነቱም የሚመነጨውና የሚረጋገጠው በመንፈስ ቅዱስ የሚመራ፣ የመንበረ ሐዋርያት ወራሽ በመሆኑና ውሳኔዎች ሁሉ ይግባኝ የሌለባቸው ከመሆኑ ላይ ነው፡፡ ሐዋርያት ከክርስቶስ፤ ሐዋርያነ አበውና ሊቃውንት ከሐዋርያት፣ እኛም ከእነዚህ ሁሉ የወረስናቸውን መሠረተ እምነት፣ ሥርዐተ አምልኮና ትውፊት የሚጠብቅና የሚያስጠብቅ ዐቃቤ ሃይማኖት ነው፡፡

 

በዚህ መነሻነት የመንበረ ሐዋርያት ወራሽ የሆነው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት በዓመት ሁለት ጊዜ ይሰበሰባል፡፡ በጥቅምትና በግንቦት ርክበ ካህናት፡፡ በሁለቱም ጉባኤያት በመንፈስ ቅዱስ መመራቱንና የመንበረ ሐዋርያት ወራሽ መሆኑን የሚያረጋግጡ ውሳኔዎች እንዲያሳልፍ ይጠበቃል፡፡ የሚወሰነውም ውሳኔ እንከን እንዳይኖርበት በፍጹም መንፈሳዊነት ተገቢ ጥንቃቄም እንዲያደርግ ይጠበቃል፡፡

 

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ በዓመት ሁለት ጊዜ መደበኛ ስብሰባ እንዲሁም እንደ አስፈላጊነቱ ልዩ ስብሰባ በማካሄድ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቀኖና፣ አመራር፣ አስተዳደር፣ እርምጃና ፖሊሲ ሁሉ የሚወሰን የመጨረሻው አካል እንደመሆኑ ምልዐተ ጉባኤው ፍሬያማና ውጤታማ ተግባራት የሚከናወኑበት ሊሆን እንደሚገባም ይታመናል፡፡

 

በዚሁ መሠረት ቤተ ክርስቲያናችን በምልዐተ ጉባኤው ውሳኔና የውሳኔ አፈጻጸም ተጠቃሚ መሆኗ እንዲረጋገጥ አጥብቀን እንሻለን፡፡ በተነጻጻሪም ከጥቅምት 12 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ እንደሚካሔድ የሚጠበቀው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ይህን እውን ሆኖ እንዲያሳየን ይጠበቃል፡፡ አጀንዳውም ከዚህ አንጻር ቢቃኝ ተገቢ ነው፡፡

 

በዚህ የአጀንዳ ቅኝት ተገቢነትና ወቅታዊነት አግባብ በአጀንዳነት ተወያይቶበት ውሳኔ እንዲያሳልፍባቸው እንደ ልጅነት የምንሻቸው አጀንዳዊ ውሳኔዎች ውስጥ ዐበይቶቹ በአምስት ሊቀመጡ ይችላሉ፡፡ እርቀ ሰላምና የስድስተኛው ፓትርያርክ ሹመት አጠቃላይ አፈጻጸም፣ ሕገ ቤተ ክርስቲያን የሚሻሻልበትንና ቤተ ክርስቲያናችን ቋሚ የምርጫ ሕግ ባለቤት የምትሆነበትን አገባብ መወሰን፤ ተግባሩና ሓላፊነቱ በግልጽ የተቀመጠለት የቴክኒክ አካል መሰየምና በአምስተኛ ዘመነ ፕትርክና በይደር በተያዙ አጀንዳዎች ላይ ተወያይቶ እንዲወሰን የቤተ ክርስቲያን ልጅነት አሳባችንን እናቀርባለን፡፡

 

ከእነዚህም በተጨማሪ ከአምስተኛው ፓትርያርክ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ዕረፍት በኋላ በዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክነት የተሾሙት ብፁዕ አቡነ ናትናኤልም ሆኑ የቋሚ ሲኖዶሱን አፈጻጸም መገምገምና ውሳኔ ሊሰጥባቸው የሚገቡ ክስተቶች ላይም ውሳኔ ከመስጠትም በላይ ቀጣዩን የአተገባበር ፍኖተ ካርታ /Roadmap/ ተጠያቂነት በሚያጎናጽፍ አግባብ ቢያስቀምጥ ለቤተ ክርስቲያን ዕድገት ገንቢ ሚና ይኖረዋል ብለን እናምናለን፡፡

 

ምእመኑም ትናንት የቅዱስ ሲኖዶስን የምሕላ ዓዋጅ ተቀበሎ እንደመፈጸሙ ቀጣዩንም ውሳኔዎቹን መፈጸም ይገባዋል፡፡ ከአባቶቻችን ጎን በመሆን የልጅነት ድርሻውን ቢወጣ እንላለን፡፡

 

ቤተ ክርስቲያናችን በኲለንታዋ ወደቀደመ ክብሯና ልዕልናዋ እንድትመለስ የምልዐተ ጉባኤው ድርሻ በሙቀተ መንፈስ ቅዱስ ዘመኑን የዋጀ ውሳኔ መወሰንና አተገባበሩን መከታተል፤ የቤተ ክህነቱ መዋቅር ድርሻ ውሳኔዎቹን ማስፈጸምና ምቹ መደላድል መፍጠር ሲሆን የምእመኑ ድርሻ ደግሞ ለውሳኔው ተፈጻሚነት ምልዐተ ጉባኤውንም ሆነ የቤተ ክህነቱን መዋቅር በሁሉም መደገፍ ያስፈልጋል፡፡

 

ስለዚህ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ውሳኔን መቀበል የቤተ ክርስቲያናችን የአንዲትነት፣ ሐዋርያነት፣ ቅድስትነትና ኲላዊነት መገለጫ ነውና ውሳኔዎቹን ተግባራዊ ከማድረግ አኳያ ሁላችንም የድርሻችንን ለመወጣት ዝግጁ እንድንሆን ያስፈልጋል፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር


  • ምንጭ፡- ጽምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት ቁጥር 3 ከጥቅምት 16-30 2005 ዓ.ም.

የቃለ ዓዋዲው ማሻሻያ ረቂቅ ይመከርበት!

መስከረም 30 ቀን 2005

ሰበካ ጉባኤ በካህናትና በምእመናን ኅብረት ላይ የቆመ መሠረታዊ የቤተ ክርስቲያናችን አስተዳደራዊና መዋቅራዊ ሥርዐት ነው፡፡ ከመንበረ ፓትርያርክ እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ባሉት መንፈሳዊና አስተዳደራዊ ጉዳዮች ላይ በየደረጃው አመራር ይሰጣል፣

 

ዕቅድ ያወጣል፣ ውሳኔ ያሳልፋል፡፡ ጉባኤው ቤተ ክርስቲያናችን ከመሬት ስሪት ተነሥታ በሕዝብ ባለቤትነት ላይ የተመሠረተችበትና ሕጋዊ ሰውነት ያገኘችበትም የሕግ አካል ነው፡፡

 

በየደረጃው በሚያወጣቸው ዕቅዶች፣ በሚሰጣቸው አመራርና በሚያሳልፋቸው ውሳኔዎቹ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ይጠብቃል፡፡ አገልግሎቷንም የተሟላ እንዲሆን ያደርጋል፡፡ የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች በሐዋርያዊ ተግባር እንዲደራጁ በማድረግ ችሎታቸውን ተጠቅሞ ኑሮአቸውን ያሻሽላል፡፡ ምእመናንን ለማብዛትና በመንፈሳዊ ዕውቀት ጎልምሰው በምግባርና በሃይማኖት ጸንተው በክርስቲያናዊ ሕይወት እንዲኖሩ ያደርጋል፡፡

 

እነዚህን ዓላማዎቹን ከማስፈጸም አኳያ ጾታ ካህናትና ጾታ ምእመናን /ጳጳሳት፣ ቀሳውስት፣ ሊቃውንት፣ ወጣቶች/ በምልዐት የተወከሉበትም በመሆኑ አሳታፊ ነው፡፡

 

ይሁንና በአጥቢያ ሰበካ ጉባኤ ደረጃ የምእመናን ንቃተ ሕሊና እየዳበረ ቢሆንም ተሳትፎው በሚፈለገው ደረጃ እያደገ አይደለም፡፡ ሰበካ ጉባኤ በወረዳ ቤተ ክህነትና በመንበረ ጵጵስና አካባቢ የተረሳም ይመስላል፡፡ በየዓመቱ የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ቢካሔድም፤ በጉባኤውም አልፎ አልፎ ሥልጠናዎች መስጠታቸው ቢበረታቱም ወደ መሬት የማይወርዱ ወደ ተግባር የማይለወጡ መሆናቸውን እንረዳለን፡፡

 

ዘንድሮም ከጥቅምት 6-11 ቀን 2005 ዓ.ም ጀምሮ ሠላሳ አንደኛው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በጽርሐ መንበረ ፓትርያርክ ይካሔዳል፡፡ እናም ተገቢ /የካህናት፣ የወጣቶችና የምእመናን/ የውክልና ተሳትፎው እንዲጠበቅ፣ ከተለመደው ሪፖርታዊ መግለጫ በዘለለ ቁም ነገራዊ አጀንዳ ተኮር ቢሆን፤ አጀንዳዎቹ በወቅታዊና ዘላቂ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ፣ አወያይና አሳታፊ ሊሆኑ ይገባል እንላለን፡፡

 

ከሪፖርት አቀራረብ ጋር በተያያዘም የአህጉረ ስብከት ሪፖርት በጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ተጠቃሎ ቢቀርብና የቁጥጥር አገልግሎት ሪፖርት ተጠያቂነትንና ግልጽነትን ከማስፈን አኳያ ራሱን ችሎና ለብቻው ተለይቶ ቢቀርብና ተገቢ የሆነ ውይይትም ሊደረግበት ይገባል፡፡

 

በዘንድሮው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በቃለ ዐዋዲው ማሻሻያ ረቂቅ፣ ተቋማዊ ማሻሻያ (Structural Reform)፣ በዕርቀ ሰላሙ እውንነት ላይ፣ በፓትርያርክ ምርጫ አፈጻጸም ሥርዐት ላይ አተኩሮ እንዲወያይና የውሳኔ አሳብ ለቅዱስ ሲኖዶስ እንዲያሳልፍ ቢደረግ፤ ከአምስተኛው ፓትርያርክ ዕረፍት በኋላ ቤተ ክርስቲያኒቱ ያለችበትን ነባራዊ ሁኔታ የሚያሳይና በቀጣይነት ሊደረጉ የሚገባቸውን የሚጠቁም ሰነድ በዐቃቤ መንበሩ የሚመራው ኮሚቴ አዘጋጅቶ የጉባኤው ተሳታፊ እንዲወያይበት ሊደረግ ይገባል፡፡ ጉባኤው ዕቅድና በጀት መትከል ቢጀምር፣ የክትትልና ቁጥጥር ሥልትን አቅጣጫ ቢበይን ለቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ ዕድገት ጠቃሚ መሆኑን እናምናለን፡፡

 

ሌላው ቢቀር እንኳን የቃለ ዓዋዲው ማሻሻያዎች ላይ የመንበረ ፓትርያርክ ሠላሳ አንደኛ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ተሳታፊዎች እንዲመክሩበትና እንዲያዳብሩት ዕድሉ ሊሰጣቸው ይገባል፡፡

 

ይህን ስንል የቃለ ዓዋዲው መሻሻል የአሁኑንና የቀጣዩን ዘመን የቤተ ክርስቲያናችንን ሐዋርያዊ አገልግሎት፣ ርምጃ ለማስቀጠል የላቀ አዎንታዊ ተፅዕኖ ያለው መሆኑን በመገንዘብ ነው፡፡

 

በዚህ መልኩ የቃለ ዓዋዲው መሻሻል ተግባራዊ መሆን ለመዋቅር ማሻሻያችን መርሕ ይሆናል፤ የሕግ አውጪውን፣ ሕግ አስፈጻሚውንና የሕግ ተርጓሚውን ተግባር፣ ሥልጣንና ሓላፊነት በመለየት፡-

 

  • ተጠያቂነትና ግልጽነት እንዲሰፍን፣
  • የቤተ ክርስቲያናችን ሀብት /የሰው ኀይል፣ የገንዘብና ንብረት/ በአግባቡ ጥቅም ላይ እንዲውል፣
  • ቤተ ክርስቲያናችን በመንፈሳዊነት ምሳሌያዊ የሆነችና ሞራላዊ የበላይነት ያላት ተቋም እንድትሆን /በብኩንነት፣ ምዝበራና ዘረፋ ላይ/ ያስችላታል፡፡

 

በዓለም አቀፍም ደረጃ /በውጭው ዓለም/ ላለችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም የበለጠ የመስፋፋትና የአንድነት በርን ይከፍታል እንላለን፡፡

 

ስለዚህ የዘንድሮ የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በቃለ ዓዋዲው ማሻሻያ ላይ ለመምከር ባለቤትም፣ ባለሥልጣንም ነውና ይመለከተዋል፡፡ አሁን ባለንበት ሁኔታ ከዚህም የተለየ፣ ከዚህም የበለጠ አጀንዳ ሊኖረው አይገባም፡፡ ቢያንስ ቢያንስ በቃለ ዐዋዲው ማሻሻያዎች ላይ ይምከር! ማሻሻያዎቹን ያዳብር! እንላለን፡፡

 

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት ቁጥር 2  ከጥቅምት 1-15 ቀን 2005 ዓ.ም.

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ለቤተ ክርስቲያናችን አንድነት ዕርቅና ሰላም መሠረት ናቸው

መስከረም 22 ቀን 2005 ዓ.ም.


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዘመኑ የተለያዩ ፈተናዎች የተፈራረቁባት ሲሆን ቤተ ክርስቲያኒቱ የእግዚአብሔር ማደሪያ ነችና የመጣውን የፈተና ጎርፍና ነፋስ ሁሉ ተቋቁማ አሁን ላለንበት ዘመን ደርሳለች፡፡ የዐላውያን ገዢዎችን ሰይፍ ከውስጥም ከውጭም የነበሩ መናፍቃንን ቅሰጣ ተሻግራ እስከአሁን የሐዋርያትን፣ የቅዱሳን ሊቃውንትን የአትናቴዎስን የቄርሎስን ሃይማኖት ይዛ ተገኝታለች፡፡፡ ስለዚህም ቤተ ክርስቲያን የሚመጡባትን ፈተናዎች የምታደንቅ፣ በዚያም ተስፋ የምትቆርጥ አይደለችም፡፡ ሁል ጊዜም ቢሆን የገሃነም ደጆች የሚሰብቁት ግልጽና ስውር ጦር እንዳለ ስለምታውቅ ከሚመጣው ፈተና ሁሉ አሸንፋ ትወጣ ዘንድ ወደ አምላኳ ትለምናለች እንጂ፡፡

 

በዚህ ባለንበትም ዘመን ቤተ ክርስቲያናችን ካጋጠሟት ከባድ ፈተናዎች አንዱ ለሃያ ዓመታት ያህል የቆየው የአባቶች መለያየት ጉዳይ ነው፡፡ እንዲህ ያሉ ታሪኮች በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ እንግዳ ነገር ባይሆኑም የሚያስከትሉት ጉዳት ግን ቀላል የማይባል ነው፡፡ በማወቅም ባለማወቅም ከውስጥ ወይም ከውጪ በሆኑ ምክንያቶች እንዲህ ያሉ መለያየቶች ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡ ዋናው ነጥብ ግን ከርስትና በሃይማኖት ምክንያት ካልሆነ በቀር ለመለያየት፣ መንጋን ለመበተን ወይም ለመከፋፈል የሚያበቃ ሥነ ኅሊና /ሞራል/ የሚሰጥ ሃይማኖት አይደለም፡፡ ሃይማኖታችን ተስፋ እንድናደርግ የሚነግረንን የእግዚአብሔር ጸጋ ሁሉ መንግሥቱንም ማግኘት የሚቻለው የዕርቅና ሰላም ሕይወት ሲኖረን ነው፡፡ ጌታችን “እኔ እንደወደድኳችሁ እርስ በእርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ ትእዛዜ ይህች ናት” እንዳለ የሕጉ ሁሉ ፍጻሜ ነው፡፡ /ዮሐ.15፥12/ እርስ በእርስ ብቻም ሳይሆን ብንችል ከሁሉም ጋር በሰላም እንድንኖር ታዘናል፡፡ ያለሰላምና ፍቅር ቤተ ክርብስቲያንን ማነጽ ማጽናትም አይቻልም፡፡

 

በ1983 ዓ.ም. ጀምሮ ቤተ ክርስቲያናችን ያጋጠማት መከፋፈል ከግብጽ ቤተ ክርስቲያን ሞግዚት አስተዳደር ነጻ ወጥተን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በተመሠረተው መንበረ ፓትርያርክ ጥንካሬ እና አሠራር ላይ ጥያቄም የሚያስነሣ ሆኗል፡፡ በቤተ ክርስቲያን የውጪና የሀገር ውስጥ የአገልግሎት እንቅስቃሴዎችም ላይ ተፅዕኖ ማሳደሩ አልቀረም፡፡ ቤተ ክርስቲያን የሲኖዶሱ፣ የስደተኛው፣ የገለልተኛው ወዘተ እየተባለች ሁሉም እንደፈቃዱ የሚኖርባት ሆና ቆይታለች፡፡

 

እነዚህ ነገሮች ዕረፍት የነሧቸው የተለያዩ ወገኖችም በአባቶች መካከል ያሉ ችግሮች እንዲፈቱ የተለያዩ ጥረቶች ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡ ይሁን እንጂ ችግሮቹ እልባት አግኝተው ቤተ ክርስቲያኒቱ ወደቀድሞው አንድነቷ ሳትመለስ በሂደት ላይ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ዐረፉ፡፡ የእርሳቸው ዕረፍትን ተከትሎም ችግሮቹ የበለጠ እንዳይወሳሰቡና መቋጫ ሳያገኙ ወደባሰ ቀውስ፣ አለመረጋጋትና ማባሪያ ወደሌለው መወጋገዝ እንዳይገባ እስከቀጣዩ ፓትርያርክ ሢመት ድረስ አስፈላጊውን ሁሉ ጥረት ከመቼው ጊዜ በላቀ ሁኔታ እንዲቀጥል ብፁዓን አባቶችን ጨምሮ ሁሉም ወገን ግፊት እያደረገ ነው፡፡

 

አገልግሎቱን አጠናክሮ የቤተ ክርስቲያኒቱን መልካም ነገር ሁሉ ማየት ዋነኛ ግቡ የሆነው ማኅበረ ቅዱሳንም የቤተ ክርስቲያናችን አንድነት ጉዳይ በእጅጉ ያሳስበዋል፡፡ መለያየቱ በሚሰጠው አገልግሎት ላይ ከፍተኛ ጫና ማሳደሩን በተጨባጭ ያየው ማኅበረ ቅዱሳን ለሁሉም የቤተ ክርስቲያን የአገልግሎት ቤተሰቦች ጉዳዩ አንገብጋቢ መሆኑን ይረዳል፡፡

 

በዚህ መለያየት ውስጥ ዓላማቸውን ለመፈጸም ይጥሩ የነበሩ ግለሰቦችና ቡድኖች በቤተ ክርስቲያናችን መዋቅር ውስጥ ለመንሰራፋትም ይውተረተሩ እንደነበር ይታወቃል፡፡ አገልግሎታችንም በሚፈለገው ደረጃ በፍጥነት ሄዷል ማለት አይቻልም፡፡ በርካታ ምእመናን በመናፍቃን ተወስደዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን የሚፈለገውንም ያህል ሀገራዊ አስተዋጽኦ ስታደርግ ቆይታለች ለማለት አያስደፍርም፡፡

 

ሌሎች ምክንያቶችም እንዳሉ ሆነው ይኸው በአባቶች መካከል ያለው መለያየትም ከላይ ለዘረዘርናቸው ውስንነቶች የራሱ አስተዋጽኦ ነበረው፡፡ መንበረ ፓትርያርክና ቅዱስ ሲኖዶስ ከአንድ ሺሕ ስድስት መቶ ዓመታት በኋላ ከግብጽ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊ ቁጥጥር ተላቀው ያገኙትን መንፈሳዊ ሥልጣንና መንበር በተሻለ አሠራር ወደላቀ የአገልግሎት አቅም የሚያደርሱበትን ሁነኛ ጊዜዎች በእነዚህ መለያየቶች ምክንያት አባክነዋል ማለት ይቻላል፡፡ የተሻለ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት መስፋፋት ማሳየት ሲቻል ወደ ኋላ ለመመለሱ አስተዋጾኦ አድርጓል፡፡ ይህ በሁሉም ልብ ያለ ሐዘን እንዲቀረፍ አባቶች ጥረት ሲያደርጉ ቢቆዩም በቀላሉ ተፈቶ ቤተ ክርስቲያንን አንድ ማድረግ ሳንችል መዘግየታችን ትውልዳችንንም የሚያስወቅስ ሆኗል፡፡

 

ይሁን እንጂ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በሕይወት እያሉ ተጀምሮ የነበረው የዕርቅና ሰላም ሂደት አሁን እልባት እንዲሰጠው የሚያስገድድ ሁኔታ ውስጥ መግባታችንን ማኅበረ ቅዱሳን ያምናል፡፡ ማኅበራችን የዕርቅና ሰላሙ ጉዳይ አስተዳደራዊ ጉዳይ ብቻም ሳይሆን የክርስቲያናዊ ሕይወትና ሥነ ምግባር ጉዳይ መሆኑ እንዲታሰብበት ይሻል፡፡ ስለዚህ አፋጣኝ እርምጃ መውሰድና ችግሩን ለመፍታት በሚያሳምን ደረጃ መንቀሳቀስ ይጠይቃል፡፡ ጉዳዩም ክብደት እንዲሰጠው ይፈልጋል፡፡ የምናገለግላት ቤተ ክርስቲያን በየምክንያቱ እየተለያየች ባለብዙ መዋቅር ስትሆን ማየት የማይታገሱት ነገር ነው፡፡ የዕርቅና የሰላም ሂደቶቹም ውጤት በግልጽ እየቀረቡ ሕዝበ ክርስቲያኑም ግፊት እንዲየደርግባቸው ይሻል፡፡

 

ለዚህም በደሙ የዋጃትን ቤተ ክርስቲያን እንዲጠብቁ ለመንጋውም እንዲጠነቀቁ አደራ የተሰጣቸው ብፁዓን አባቶች ድርሻ የጎላ ነው፡፡ ዕርቅና ሰላምን በቤተ ክርስቲያን አስፍኖ የቤተ ክርስቲያንን አንድነት ማጽናት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ለአገልግሎት የሚመች ስልታዊ አካሄድ አሠራርና አደረጃጀት እንዲሰፍን መፍቀድ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህንንም ከእግዚአብሔር የሆነውን አደራ ከመጠበቅ አንጻር፣ ለአገልግሎቱ ስኬት ከማምጣት፣ ምእመናን በአገልግሎቱ ረክተው እንዲጸኑ ከማድረግ፣ በታሪክ ውስጥ ተጠያቂ ካለመሆን አንጻር ሁሉ ሓላፊነትን ሊወጡ ይገባል፡፡

 

ሁሉም የክርስቲያን ወገን ቢሆን ሊረዳው የሚገባው የሰበሰበችን ቤተ ክርስቲያን እጅግ ታሪካዊ ባዕለጸጋና አኩሪ መሆኗን ነው፡፡ የሊቃውንቱ የቅዱስ ያሬድ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ፣ የእነ አቡነ ተክለሃይማኖት የእነ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ቤተ ክርስቲያን መሆኗን ልንረዳ ይገባል፡፡ ብዙ ዋጋ ተከፍሎባታል፡፡ ስለዚህ ክብርና አንድነቷን ዕርቅና ሰላምን በማስፈን ልናጸና ይገባል፡፡ ላለብን ችግር መፍትሔ የሚሰጠውም ፈጣሪ መሆኑን በማመን ብፁዓን አባቶችን በጸሎት መርዳት ይገባል፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱን አንድነት በጥብቅ እንደምንፈልገውም በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ መግለጽ ግፊትም ማድረግ ይገባናል፡፡ ለሚፈለገው አንድነት ደግሞ መሠረቱ ዕርቅና ሰላም ነው፡፡

 

ቤተ ክህነቱም እግዚአብሔር ያለፈውን ይቅር እንዲለን፣ ከሚመጣውም እንዲጠብቀን ስለ አንድነታችን በጸሎት ሊተጋ ይገባል፡፡ ያለፈው መልካም ያልሆነው ነገር ሁሉ ሊረሳ፣ በጎው ደግሞ ሊወሳ ይገባል፡፡ በጎ ፈቃድና ሰላምን መውደድ ከሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ የተማርነው የተረዳነው ነውና ሁሉም ወገን ያንኑ እንዲያጸና መምከር ይጠበቅበታል፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳንም በበኩሉ ከዚህ ቀደም ይዞት የቆየውን ይህንኑ አቋም አሁንም ለማስተጋባት የተገደደው ከችግሩ ወቅታዊነትና ከጊዜው አንገብጋቢነት የተነሣ ነው፡፡ ስለዚህ ችግሩ ከምንም ዓይነት መዘዝ በጸዳ ሁኔታ፣ ቀኖናዊና ሃይማኖታዊ መሠረቶች ተጠብቀው ዕርቅና ሰላምን የማስፈን እንቅስቃሴው በሚያሳምን ደረጃ ሊኬድበት ይገባል፡፡ የአባቶችና የሀገር ሽማግሌዎችም ጥረት ሊመሰገን እንደሚገባው ማኅበረ ቅዱሳን ያምናል፡፡ ውጤት እስከሚገኝ ለሂደቱ አስፈላጊውን ሁሉ አስተዋጽኦ ሊያበረክት መዘጋጀቱን ለሁሉም ወገን ሊገልጽ ይወዳል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

  • ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት 20ኛ ዓመት ቁጥር 5 2005 ዓ.ም.

ማኅበረ ቅዱሳን ትእምርተ ሰላም

መስከረም 21 ቀን 2005 ዓ.ም.


በኢትዮጵያ ከጥቂት ዓመታት ወዲህ ከሃይማኖት አክራሪነት ጋር በተያያዘ አንዳንድ ግጭቶች መከሰታቸው ይታወቃል፡፡ መንግሥትም ለችግሩ  መፍትሔ ለመስጠት ጥረት እያደረገ ይገኛል፡፡ የአብዛኛዎቹ የ”ግጭት” ጠባይ ግን የተለየ ነበር፡፡ የሁለት እምነት ተከታዮች በመፎካከርና በመወዳደር ወይም ደግሞ ከተራ ጥላቻና ግለሰባዊ ግጭት አንሥተው ሃይማኖታዊ ያደረጉት አልነበረም፡፡

 

ከዚያ ይልቅ በአንድ ወገን ያሉት በማያውቁትና ባላሰቡት ሰዓት የደረሰ ድንገተኛ አደጋ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ጥቃቱን የፈጸሙትም የሚከተሉትን ሃይማኖት አባቶች ወካዮችና ከዚያው ከቤተ እምነታቸው ተከታዮች ሙሉ ይሁንታ አግኝተው የተላኩ አልነበሩም፡፡ ይህን የማድረግ ዓላማ ብቻ ሳይሆን በቂ ዝግጅትና ጥናት ያደረጉ የሃይማኖት አክራሪዎች መሆናቸው ከድርጊታቸውም፤ ከተገኘውም ማስረጃ ግልጽ ነበር፡፡

 

በተከታታይ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ምእምናንና አብያተ ክርስቲያናት ላይ በአርሲ ዞን ቆሬ ወረዳ በአንሻ ቀበሌ፣ በጅማና ኢሉአባቦራ ጥቃት ሲያደርስ የነበረው የአክራሪ እስልምና ቡድን ኢትዮጵያዊ መልኩን አሽቀንጥሮ ጥሎ እስላማዊ ዓለም ዓቀፋዊ ግዛትን ለማፋጠንና የምሥራቅ አፍሪካ ስልቱን ለመፈጸም እንደመሰናክል ያያትን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ለማስወገድ ያለመው እንቅስቃሴው አካል እንደነበረም እንገነዘባለን፡፡

 

ይህን ተከትሎም በሕዝቡ መካከል ለዘመናት አብሮ የመኖር ባህላችንን የሚፃረር ድርጊት እየተስተዋለ ነበር፡፡ በተለይ ደግሞ በክርስቲያኑና በሙስሊሙ ማኅበረሰብ መካከል በወቅቱ ተፈጥረው የነበሩት አዳዲስ ክስተቶች በሁለቱ ሃይማኖት ተከታዮች መካከል የማያባሩና መቆሚያ የሌላቸው ግጭቶች መፍጠር ዓላማ አድርገው የሚንቀሳቀሱ ባዕዳን ኀይሎች በአምሳላቸው የወለዷቸው አክራሪዎች የሚመሩት እኩይ ድርጊት መሆኑም ድርስ ነበር፡፡ ከጥቃቱ በኋላም መንግሥት ተገቢውን ትኩረት በመስጠት የተለያዩ የማስተማርና ሕግ የማስከበር ሥራዎችንም ሲሠራ እንደነበረም በሚገባ እናውቃለን፡፡

 

ትናንትም ሆነ ዛሬ ምልክቱ ሰላም እንጂ “አክራሪነት” ያልሆነው ማኅበረ ቅዱሳን ሀገራዊ ድርሻውን በሦስት መልኩ ተወጥቷል፡፡ የመጀመሪያው ከመጀመሪያው ጀምሮ ምእመናን አክራሪውን፣ ነባሩንና ሰላማዊውን እስልምና ነጥለው እንዲመለከቱ ከፍተኛውን ድርሻ ተወጥቷል፡፡ ሁለተኛ አክራሪዎቹ ለሚያነሷቸው ታሪካዊና ዶግማዊ ጥያቄዎች በተጻፉት ጽሑፎች መጠንና ቁጥር ጋር ሊነጻጸር ቀርቶ እዚህ ግባ የሚባል ባይሆንም መጠነኛ ምላሾችን ሰጥቷል፡፡ ሦስተኛ ተቻችሎና ተከባብሮ ስለመኖር ከየትኛውም አካል በፊትና በከፍተኛ ሽፋን ሠርቷል፡፡ ስለ አክራሪ እስልምናና ስለትንኮሳው እጅግ አነስተኛና ክስተት ተኮር የሆኑ መረጃዎችን በመስጠት ችግሩ ሲያጋጥም ለመንግሥት ማመልከት እንደሚገባ አቅጣጫ ለማሳየት ሞክሯል፡፡

 

ማኅበሩ ይህን በወቅቱ ያደረገው አንድን ነገር እየሰሙ እንዳልሰሙና እንደሌለ ከመቁጠር ይልቅ ችግሩን በትክክል አሳውቆ ለመፍትሔው መሥራት ይገባል ብሎ ስለሚያምንና መንግሥት በወቅቱ አክራሪነትን ለመግታትና ግጭቶችን ለማስወገድ እያደረገ የነበረውንም ጥረት የማገዝ ሀገራዊ ግዴታንም ከመወጣት አንጻር መሆኑንም ለመግለጽ እንወዳለን፡፡

 

ይሁንና ለቤተ ክርሰቲያኒቱ ተጨማሪ አስተዋጽኦ አበረክታለሁ ብሎ የተደራጀውንና ከሰላማዊ ባሕርይው በመነጨ የሃይማኖት አክራሪነት በጽናትና በአቋም እየታገለ ያለውን ማኅበረ ቅዱሳንን በተሳሳተ መረጃ በአክራሪነት የመፈረጅ አዝማሚያዎች በአንዳንድ አካላት እየታዩ መሆናቸውንም እንረዳለን፡፡

 

በማያወላዳ ሁኔታ ማኅበረ ቅዱሳን ትናንትም ሆነ ዛሬ የሃይማኖት አክራሪ አለመሆኑንና ማንንም ወደ ሃይማኖት አክራሪነት የሚመራ ተቋም አለመሆኑን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡ የሃይማኖት ሥርዓታችንን አጥብቀን በመፈጸማችን እንታወቅ ይሆናል እንጂ የአክራሪነት ውጤት በሆኑት ጸብና ግጭት አንታወቅም፡፡ ያለ ስም ስም መስጠትና በተሳሳተ መረጃ መፈረጁ አንዳች መፍትሔ ሊሰጠው እንደሚገባ በጽኑ እናምናለን፡፡

 

ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሃይማኖት አክራሪነትን አስመልክተው ለምክር ቤቱ አባላት ሲገልጹ ከሕዝብና ቤት ቆጠራ ውጤት ጋር አያይዘው “….አንዳንድ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት….” ብለው መጥራታቸውን እንደምቹ አጋጣሚ የወሰዱ የማኅበሩን አገልግሎት የማይወዱና ምናልባትም ማኅበሩ ባይኖር በቤተ ክርስቲያኒቱ መሠረተ እምነት፤ ሥርዓተ አምልኮና ትውፊት ላይ የፈለጉትን ማድረግ የሚቻላቸው የሚመስላቸው አካላት የማኅበሩን ስም ማጥፋታቸውን እንደቀጠሉ ናቸው፡፡

 

እነዚህ ወቅታዊ ፓለቲካዊ ሁኔታዎችን የሚንተራሱ የተሐድሶ መናፍቃን አቀንቃኞች ከዚህ በፊት ከቅዱስ ሲኖዶስ ጋር ለማጣለት፣ ከሌሎችም አካላት ጋር በማጋጨት እየደከሙ ሳይሳካላቸው ሲቀር ደግሞ የወቅቱን የፓለቲካ ነፋስ ተጠቅመው መንግሥታዊ አካላትን በማሳሳት በማኅበረ ቅዱሳን መቃብር ላይ ቆመው ቅዠታቸው እውን ሆኖ ለማየት ሲባዝኑ እያስተዋልንም ነው፡፡ ስለዚህም መንግሥታዊ አካላት በእነዚህ አካላት በደረሳቸው የተሳሳተ መረጃ ተመሥርተው ማኅበሩን ከመፈረጃቸው በፊት በቂ ጥናትና አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንደሚያደርጉም እምነታችን ነው፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን በግልጽና በይፋ ከሚሠራው ሥራ ውጭ በስውር የሚሠራው አንዳች ነገር የለም፡፡ ሥራዎቹን ከሌሎች ሥራዎች ጋር ማጥናትና በንጽጽር መመልከት እውነታውን ለመረዳት በእጅጉ ይጠቅማል፡፡ ከዚህ አልፎ ግን በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ በግልጽም ሆነ በስውር ሊያደርሱት የፈለጉትን የሃይማኖት ብረዛና ክለሳ ያልተሳካላቸው አጽራረ ቤት ክርስቲያን በሚሰጡት የተሳሳተ መረጃ ተመሥርቶ ትእምርተ ሰላም /የሰላም ምልክት/ የሆነውን ማኅበር መፈረጅ አይገባም፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን በቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር ሥር ያለ የቤተ ክርስቲያኒቱን አስትምህሮና መሠረተ እምነት የሚጠብቅ፣ በራሱ አቅምም መሠረት የማስጠበቅ ድርሻውን የሚያበረክት፣ በቅዱስ ሲኖዶስ የጸደቀ ደንብ የተሰጠውና በእርሱም መሠረት ብቻ የሚሠራ ማኅበር እንጂ ራሱን የቻለ የእምነት ሴክትም አይደለም፡፡

 

አባላቱም በአብዛኛው ከፍተኛ ትምህርት የተማሩ፣ በሀገሪቱ ተቋማት ውስጥ ታላቅ ሀገራዊ ሓላፊነትን የሚወጡ፣ ከፊሎቹም በከፍተኛ የሓላፊነት ቦታዎች ላይ ያሉ፣ ለሀገርና ለሕዝብ በሚሰጠው አገልግሎትም ሓላፊነት የሚሰማቸው ዜጎች እንጂ ከክርስትናው አስተምህሮም ሆነ ከኅሊና የተነሣ የማያደርጉትንና ሊያደርጉም የማይችሉትን አክራሪነት ለማኅበሩ አባላት መስጠት አይገባም እንላለን፡፡

 

መንግሥት እንደ ሀገር መሪነቱ የእምነት መሪዎችን ቀርቦ ማወያየቱ፣ ብቅ ጥልቅ፣ ብልጭ ድርግም የሚሉ የእምነት ነክ “ግጭቶች” ለማስወገድ የሚያደርገው ጥረት በሚያስመሰግነውም የችግሩ ሰበዝ ከየት እንደሚመዘዝና የተፈጠረውንም ችግር ከመሠረቱ ለመፍታት ጉዳዩን በጥልቀት ከሚያውቁት ወገኖች መረጃ የመሰብሰቡን ሥራ አጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል፡፡

 

በሀገራችን አሁን ምልክቱ በጉልህ እየታየ ያለው የሃይማኖት አክራሪነት እንቅስቃሴ በብዙኃኑ የክርስትናውም ሆነ የእስልምናው ተከታይ ዘንድ ተቀባይነት የሌለው ተግባር ነው፡፡ የዚሁ አካል የሆነው ማኅበረ ቅዱሳንም እንደ ትናንቱ ሁሉ ዛሬም ጥብዓት በተሞላው ቁርጠኝነት የሚታገለው ነው፡፡ በመሆኑም መንግሥት አሁን እያደረገ ያለው የፀረ አክራሪነት ትግል እንደተጠበቀ ሆኖ በትክክል የአክራሪነት ጠባዩ ከየትኛው አቅጣጫ እንደመጣና ምንጩ የትና ምን እንደሆነ በመለየት ትክክለኛውን ብያኔ ሊሰጥ ይገባል እንላለን፡፡

 

በአንዳንድ አካላት የተሳሳተ አቻ ለመፍጠር ሲባል በጥቅል ለሃይማኖት ተቋማትና ተከታዮቹ የሚቀመጠውም ፍርጃ ሊስተካከል እንደሚገባውና በተገቢው አካል ተገቢውን ሥዕል ማግኘት እንዳለበትም እምነታችን ነው፡፡

 

በመጨረሻም ማኅበረ ቅዱሳን አክራሪነትን እንደሚያወግዝ አበክረን እንገልጻለን፡፡ በተጨማሪም ማኀበሩ ከዚህ በፊት እንዳደረገው ሁሉ ሰላምን አንግቦ ስለ ሰላም ከመንግሥትና መንግሥታዊ ካልሆኑም ሆነ ከሌሎች የሃይማኖት ተቋማት ጋር ለመሥራት ከመቼውም ጊዜ በላይ ዝግጁ መሆኑን ለመገለጽ እንወዳለን፡፡ በዚህም ትልቅ ሀገራዊ ሓላፊነትንና የዜግነት ድርሻውን በመወጣት አመርቂ ውጤት እንደሚያስመዘግብም ያምናል፡፡

 

ወስብሐት ለግእግዚአብሔር


  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ 19ኛ ዓመት ቁጥር 23 2004 ዓ.ም.

መጪውን ጊዜ በሃይማኖት “ብሔርተኝነት” መዋጀት

መስከረም 18 ቀን 2005 ዓ.ም.


ጊዜ ይመጣል ጊዜ ይሄዳል፡፡ ጊዜ መጥቶ ሲሄድ ግን እንደው ዝም ብሎ አይደለም፡፡ የጊዜውን አሻራ አሳርፎ ነው፡፡ አሻራው ግን አዎንታዊም አሉታዊም ሊሆን ይችላል፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ ምርጫው በጊዜ መጠነ ክበብ ውስጥ ያለው የሰው ልጅ ነው፡፡

 

የሰው ልጅ ደግሞ በጊዜያት ውስጥ የረቀቀና የገዘፈ ዓለም ባለቤት ሆኖ የተፈጠረና ጊዜ የማይቆጠሩላቸው የሥሉስ ቅዱስ ፍጡር ነው፡፡ በሕያውነቱ ረቂቁን ዓለም- ዓለመ ነፍስን መስሎና ሆኖ ሲኖር፤ በምድራዊነቱ ግዙፉን ዓለም- ዓለመ ሥጋን በተዋሕዶ ነፍስ መስሎና ሆኖ ይኖራል፡፡ በዚህም የሁለት ዓለም ባለቤት ነው፡፡ የሰማያዊና ምድራዊ ወይም የመንፈሳዊና ዓለማዊ፡፡

 

እንዲህ ሆኖ ሲፈጠር በነጻ ምርጫው እንዲኖር የሚያስችለው ነጻ አእምሮ የተቸረው ብቻ ሳይሆን የምርጫውን ተገቢነትና ትክክለኛነት የሚያረጋግጥበት አእምሮ የተሰጠውም ባለጸጋ ፍጡር መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

 

በረጅሙ የጊዜ ሂደት ውስጥ ከግዙፉ ዓለም- ዓለመ – ሥጋ፤ ግፊት አንጻር መውደቅ መነሣቱ አይቀሬም ነው፡፡ ትልቁ ቁም ነገርም መውደቁ ሳይሆን ወድቆ አለመቅረቱ – መነሣቱ ነው፡፡ ሃይማኖተኛ የሚያሰኘውም ይኼው የመነሣት ጉዞ አካል የሆነው መንፈሳዊነቱ ነው፡፡

 

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምትገለገለውም የምትጎዳውም በዚሁ ፍጡር ነው፡፡ የመውደቅ መነሣቱም ሰንኮፍ አሐቲ፣ ቅድስት፣ ሐዋርያዊት፣ ኲላዊት ቤተ ክርስቲያናችን ላይ በአዎንታዊም ሆነ በአሉታዊ ጥላውን ማሳረፉ አይቀሬ ነው፡፡

 

በዚህ ወቅት በምድር ያለችው ሰማያዊ ቤታችን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በልዩ ልዩ ሰብዓዊ ግፊት በወለዳቸው እኲያት እየተፈተነች ነው፡፡ ከውጪ ከሥጋ በሆኑ በሉላዊነትና የዚህ ውጤት በሆኑት በዘመናዊነት፣ ዓለማዊነት፣ ለዘብተኝነት እየተፈተነች መሆኑን እንገነዘባለን፡፡

 

በተለይ ከሰሞኑ ከፓትርያርክ አሰያየም ጋር ተያይዞ ለአስቀመጡት የጥፋት ግብ አባቶችን፣ ሊቃውንቱንና ምእመኑን ለመከፋፈል ዓላማ እንዲረዳቸው አጽራረ ቤተ ክርስቲያን ወንዛዊነትን – ጎጣዊነትንና – ዘውገኝነት የቤተ ክህነነቱ ባሕርያዊ ቁመና ለማድረግ ሲውተረተሩ መገንዘብ ችለናል፡፡

 

እነዚህ የክፍፍልና የልዩነት ዐውድማዎች የከፋ ጥፋት ከማድረሳቸው በፊት የሃይማኖት “ብሔርተኝነት” በወለደው ጥብዓት በቃችሁ ሊባሉ ይገባል፡፡ የሃይማኖት ብሔርተኝነት መነሻው አገራችን በሰማይ፤ ኑሮአችን በዓለመ ነፍስ ከመሆኑ ላይ ነው፡፡ የሃይማኖት ብሔርተኝነት ሲባልም ሃይማኖትን በሃይማኖት እናት፣ አባትና ብሔር አድርጎ መውሰድ ወይም በአጭሩ የሃይማኖት ወገንተኛ ማለት ነው፡፡ ከዚህም የተነሣ የሃይማኖት “ብሔርተኝነት” ወንዝ- ጎጥና- ዘውግ ዘለል መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

 

የሃይማኖት “ብሔርተኝነት” በቤተ ክርስቲያናችን የነበረና የቆየ ማእከለ አንድነት እንጂ አዲስ ክስተት አይደለም፡፡ ለዚህም ትንታኔያችን ማሳያው ሁለት ነው፡፡

 

የመጀመሪያው ምድረ ሙላዱ /መካነ ሙላዱ/ ከኢትዮጵያ ያልሆነው እና ከኢትዮጵያ ተልኮ ሄዶ ከእስክንድርያው ፓትርያርክ በቅዱስ አትናቴዎስ ዘንድ ኤጲስ ቆጶስ ሆኖ ተሾሞ የመጣው ቅዱስ ፍሬምናጦስ አባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ነው፡፡ በአራተኛው መቶ ዓመት “ቅዱስና ያለ ተንኮል የሚኖር ነውርም የሌለበት ከኀጢአተኞችም የተለየ ከሰማያትም ከፍ ያለ እንደዚህ ያለ ሊቀ ካህናት ይገባናል” /ዕብ.7፥26/ ብሎ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ስለ ክርስቶስ ሊቀ ካህንነት እንደተናገረው፤ ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስ ከሾማቸው ከሐዋርያት ሐረገ ክህነት ተያይዞ የመጣ የሐዋርያት ተከታይ የሆነ ሊቀ ካህናት ማግኘት ይገባል ብላ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጳጳስ እንዲያስመጣላት ቅዱስ ፍሬምናጦስ አባ ሰላማን ወደ እስክንድርያ ስትልክ በሃይማኖት “ብሔርተኝነት” እንጂ በወንዛዊ- በጎጣዊ- በዘውጋዊ ብሔርተኝነት አይደለም፡፡ ቅዱስ አትናቴዎስ የእስክንድርያው ፓትርያርክም ራሱኑ /ቅዱስ ፍሬምናጦስን/ ሾሞ የላከው በጎጠኝነት- በዘውገኝነት- በወንዘኝነት ሳይሆን በሃይማኖት ብሔርተኝነት መሆኑን ማስታወስ እንወዳለን፡፡

 

ሁለተኛው ምድረ ሙላዳቸው ከኢትዮጵያ ያልሆኑ በአምስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን /479 ዓ.ም. አካባቢ/ የሮማ ግዛት ከነበሩ ልዩ ልዩ አገሮች ዘጠኝ ቅዱሳን ወደ አገራችን መምጣት ነው፡፡ ተሰዐቱ ቅዱሳን በእምነት መሰሎቻቸው የሆኑ ክርስቲያኖች ወደሚኖሩባት ሀገር ወደ ኢትዮጵያ ተሰደው ሲመጡ ከነትምህርታቸው ቅድስናቸውን የተቀበልነው፤ እነርሱም በስደት በሚኖሩበት አገር ሥርዐተ ምንኩስናን ያስፋፉት፤ ገዳማዊ ሕይወትንና ምናኔን ያስተማሩት፣ ገዳማትን በየቦታው ያቋቋሙትና ያልተተረጎሙትን መጻሕፍት ወደ ግእዝ የተረጎሙት በሃይማኖት “ብሔርተኝነት” እንጂ በወንዛዊ- ጎጣዊና- ዘውጋዊ ብሔርተኝነት አለመሆኑን ማስታወስ እንፈልጋለን፡፡

 

በዚህ መልኩ የመጣውን ሥርዐተ ሢመት በሥጋዊና በደማዊ ፍላጎት ማጉደፍ ሥርየት የሌለው በደል ነው፡፡ ትናንት አባቶቻችን በሃይማኖት “ብሔርተኝነት” ቤተ ክርስቲያናችን በግብጽ ቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር ጥገኝነት ተላቃ ራሷን እንድትችልና ከራሷ የቤተ ክርስቲያን መሪዎችን እንድትሾም ብርቱ ተጋድሎ ያደረጉት በወንዛዊ- ጎጣዊና- ዘውጋዊ ብሔርተኝነት እንድንራኮትበት ሳይሆን በሃይማኖት ብሔርተኝነት ወደ ተሻለ ምዕራፍ እንድናሸጋግራት ነበር፡፡

 

ትናንት አባቶቻችን በወንዝ- በጎጥ- በዘውግና ቋንቋ ሳይቧደኑና ሳይደራጁ በሃይማኖት ብሔርተኝነት ጳጳሳትን ሾመዋል፤ ሞያና ሞያተኛን አገናኝተው የአገልግሎት ምደባ አድርገዋል፡፡ ከብሔርና ነገድ በላይ ለሃይማኖት ብሔርተኝነት ተገቢውን ዋጋና ክብር ሰጥተው ቤተ ክርስቲያናቸውንና መንጋቸውን በጥብዓት በመንኖ ጥሪትና በትግሃ ሌሊት አገልግለው ላያልፉ አልፈዋል፡፡

 

አስቀድመን ለመግለጽ እንደሞከርነው ዛሬ ከሃይማኖት “ብሔርተኝነት” ይልቅ ወንዛዊ- ጎጣዊ- ዘውጋዊ ብሔርተኝነቱ ገንኖ ወጥቷል፡፡ ብርቱ የተባሉትን ሁሉ እየቆረጠ ሲጥል እያስተዋልንም ነው፡፡ በዚህም የተነሣ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ ሢመት የሚታጩ አበው መንፈሳዊ ሕይወታቸው፣ ሞያዊ ብቃታቸው፣ የአመራር ክሂሎታቸው፣ ዐቃቤ ሃይማኖተኝነታቸው ሳይሆን ወንዛዊ- ጎጣዊ- ዘውጋዊ ተክለ ቁመናቸው መስፈርት እስኪመስል አባቶችን፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ምእመናን አቧድኖ ለማፋጀት የተዘጋጁ ወገኖች ብቅ ብቅ ማለት መጀመራቸውንም እንገነዘባለን፡፡

 

የሃይማኖት “ብሔርተኝነት” ደፍቀው ወንዛዊ- ጎጣዊና- ዘውጋዊ ብሔርተኝነት የሚያቀነቅኑ እነዚህ ወገኖች ለቤተ ክርስቲያናችን ልዕልና፣ ዕድገትና ልማት እንዲሁም ለምእመናን መብዛትና መጽናናት የሚያስቡ አለመሆናቸውን ከዚሁ ድርጊታቸው መረዳት ችለናል፡፡ ይልቁንስ ለእነርሱ ቀኝ እጅ ሆኖ፤ የእነርሱን ፍላጎት የሚያስፈጽም “የተረኞች” አባት ፍለግ ውስጥ የገቡ ሰዎች ቁመናን ገንዘብ ያደረጉ መሆናቸውንም ተረድተናል፡፡

 

ቤተ ክርስቲያኒቱ በቀኖናዋ የ”ተረኞች ፓትርያርክ” ሥርዐተ ሢመት የላትም፤ እንዲኖራትም አልተፈቀደም፡፡ ፕትርክና በወንዛዊ- ጎጣዊና- ዘውጋዊ ተረኝነት የሚገኝ ሳይሆን እግዚአብሔር ባወቀው በግብረ መንፈስ ቅዱስ የሚገኝ ሢመት መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “አንዱ እኔ የጳውሎስ ነኝ፤ ሁለተኛውም እኔ የአጵሎስ ነኝ ቢል ሰዎች ብቻ መሆናችሁ አይደለምን? አጵሎስ እንግዲህ ምንድር ነው? ጳውሎስስ ምንድር ነው? በእነርሱ እጅ ያመናችሁ አገልጋዮች ናችሁ፤ ለእያንዳንዳቸውም ጌታ እንደሰጣቸው ያገለግላሉ፡፡ እኔ ተከልሁ አጵሎስም አጠጣ፤ ነገር ግን እግዚአብሔር ያሳድግ ነበር፡፡ እንግዲያስ የሚያሳድግ እግዚአብሔር እንጂ የሚተክል ቢሆን ወይም የሚያጠጣ ቢሆን አንዳች አይደለም፡፡ የሚተክልና የሚያጠጣ አንድ ናቸው፤ ነገር ግን እያንዳንዱ እንደራሱ ድካም መጠን የራሱን ደመወዝ ይቀበላል” 1ኛ ቆሮ.3፥4-81 ያለውን በዕዝነ ልቡና መያዝናም ተገቢ ነው፡፡

 

ከዚህ አኳያ የ”ተረኝነት ሥርዐተ ፕትርክና” አስተሳሰብ ፍጹም ሥጋዊ ከመሆኑም በላይ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን እጅግ አዋራጅና ጎጂ ነው፡፡ የዚህ ፍጹም ሥጋዊ አስተሳሰብ አቀንቃኞች ከወዲሁ ራሳቸውን ተረኛ ጥቅመኛ አድርገው የሰየሙ ናቸው፡፡ መቼ ነው እኛ ደግሞ አስወጪ አስገቢ የምንሆነው? ተረኛ አሿሚ፣ አሻሪ ሆነን ቤት የምንሠራው፤ መኪና የምንገዛው ባዮች መሆናቸውንም መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

 

እንዲህ ዐይነቱ ፍጹም ሥጋዊ ቅኝት የሚያመለክተው አንድ ነገር ነው፡፡ የሃይማኖት “ብሔርተኝነት” እያጸጸ መምጣቱንና ውስጡ ጥቅመኝነት ሆኖ ሽፋኑ ወንዛዊ- ጎጣዊ- ዘውጋዊ የሆነ ብሔርተኝነት መሠረት እየያዘ መሆኑን ነው፡፡

 

እናም መጪውን ጊዜ ለቤተ ክርስቲያን የተሻለና በጎ ከማድረግ አኳያ የጊዜውን አበው፣ ሊቃውንትና ምእመን በሃይማኖት “ብሔርተኝነት” ዋጅቶ ከወንዛዊ- ጎጣዊ- ዘውጋዊ ብሔርተኝነት ደዌ መፈወስ አማራጭ የሌለው መፍትሔ ነው፡፡

 

የመጪውን ጊዜ ፓትርያርክ አሰያየምም በሃይማኖት “ብሔርተኝነት” መዋጀት በመንፈሳዊነታቸው እና በአመራር ክሂሎታቸው እንጂ በጎጣዊ- ወንዛዊ- ዘውጋዊ ማንነታቸው መሆን የለበትም እንላለን፡፡ አባቶቻችን ለቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ ሢመት መብቃት ያለባቸው በአባትነታቸው እንጂ መልክዐ ምድራዊ ብሔርተኝነት በወለደው ወንዛዊነት- ጎጣዊነት- ዘውገኝነት አይደለም፡፡

 

ለተግባራዊነቱ ደግሞ በመንፈስ ቅዱስ የሚመራው፣ የመንበረ ሐዋርያት ወራሽና የቤተ ክርስቲያኒቱ የበላይ አካል የሆነው የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት የአንበሳውን ድርሻ መውሰድ አለባቸው እንላለን፡፡

 

“አባ እገሌ “እገሌ ፓትርያርክ ይሁን” ሲል ሌላኛው ደግሞ ሞቼ እገኛለሁ አለ” እያሉ የሚያናፍሱትን ክፉ ወሬ አሉባልታ የሚያደርግ ቁርጠኝነት ከአባቶቻችን ይጠበቅባቸዋል፡፡ ከራስ ይልቅ ለቤተ ክርስቲያን ቅድሚያ እየሰጡ በሥልጣን የሚጣሉ አባቶች ሳይሆኑ ለአንዲት፣ ቅድስት፣ ሐዋርያዊትና ኲላዊት ቤተ ክርስቲያን ዓላማ በጋራ የሚሠሩ አባቶች እንደአሉን እንደሚያረጋግጡ ጽኑ እምነታችን ነው፡፡

 

ብፁዓን አበው ለሢመተ ፕትርክና ዕጩ ሆነው የሚቀርቡት አባቶቻችን መንፈሳዊ፣ ለመምራት ብቃት ያላቸውና ዐቃቤ ሃይማኖት እስከ አሁኑ ድረስ ወንዛዊ- ጎጣዊ- ዘውጋዊ ማንነታቸው ከየትም ሊሆን ይችላል የሚል ተጨባጭ መልእክት እንደሚያስተላልፉም ባለሙሉ ተስፋ ነን፡፡

 

ቤተ ክርስቲያን በቀጣይ ከባድ ግን ልትወጣው የምትችለው ፈተና አለባት፡፡ በቃላት የሚፈታና የሚነገር ሳይሆን በተግባራዊ እንቅስቃሴ የሚፈተነው፡፡ ከዚህ አኳያ ቀጣዩ ጉዞ በሃይማኖት “ብሔርተኝነት” እጅ ለእጅ መያያዝንና ጠንካራ አንድነትን የሚጠይቅ ነው፡፡ ለምን አልተጣሉም? ለምን አልተከፋፈሉም? የሚሉ አጽራረ ቤተ ክርስቲያን አርፈው የሚቀመጡበትም ሁኔታ እንደሌለ መገንዘብ ይቻላል፡፡

 

ይህን የጥፋት ሕልማቸውን እውን ለማድረግ አባቶችን ለመከፋፈል፣ በምእመናን መካከል ልዩነትን ለመፍጠር፣ ሊቃውንቱን ለማጥላላትና ቤተ ክርስቲያኒቱን ለማዳከም ጥረታቸውን እንደሚቀጥሉም ይታመናል፡፡ ብፁዓን አበውም፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንም ምእመናንም ይህን አውቀው በሃይማኖት “ብሔርተኝነት” ጠንክሮ መጓዝ ይጠበቅባቸዋል እንላለን፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር


  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት ቁጥር 1 2005 ዓ.ም.

ከምርጫው ይልቅ ለቅድመ ምርጫው!!

መስከረም 8 ቀን 2005 ዓ.ም.


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ

 

የረጅም ዘመን ታሪክ ያላት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ይህን ያህል ዘመን ተጉዛ ከዚህ የደረሰችው በተአምር ብቻ አይደለም፡፡ ሁል ጊዜ በጽኑ እምነትና ምግባር እግዚአብሔርን በማመስገንና ሰውን በማገልገል የታወቁ እልፍ አእላፍ ቅዱሳን ካህናትና ምእመናን በውስጧ በመኖራቸው ነው፡፡ በእነዚህ ቅዱሳን አበው በየቦታው ትምህርት ቤቶች እንዲስፋፉና መጻሕፍትም እንዲበዙ የተደረገውም ጥረት ለዚህ ታሪካዊ ዕድገት ያበረከተው አስተዋፅኦ የታሪክ ትዝታ ብቻ ሳይሆን አሁንም በተግባር የሚታይ ሐቅ ነው፡፡

 

በዚህ የታሪክ ጉዞ ውስጥ ሢመተ ጵጵስና በኢትዮጵያ የክርስትና ሕይወት መንፈሳዊና ማኅበራዊ የታሪክ ጉዞ ዘመናትን ያስቆጠረ ታሪክ አለው፡፡ በአራተኛው ምዕት ዓመት ሀገራችን የሙሉ ምሥጢረ ቤተ ክርስቲያን ባለቤት በመሆን ፍጹም በረከተ መንፈስ ቅዱስን ተቀበለች፡፡ በዚህም ወቅት ዛሬ ያለችው ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን በመንበረ ጵጵስና ደረጃ ተቋቋመች፡፡

 

ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ኢትዮጵያና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን እንደ ቀለምና ብራና እንደ ቃልና አንደበትም ተዋሕደው “ከኀይል ወደ ኀይል” ከክብር ወደ ክብር፣ ከበረከትም ወደ በረከት ሲጓዙም ኖረዋል፡፡ እንደገናም “በጸጋ ላይ ጸጋን ተቀበልን” እንደተባለው ከ1951 ዓ.ም. አንሥቶ ላለፉት 53 ዓመታት በታላቅ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዐት የምናከብረውን ፓትርያርካዊ ክብር ተጎናጸፈች፡፡ አክሊለ በረከትን ተቀዳጀች፤ ፓትርያርካዊ በትረ ክህነትን ጨበጠች፤ መንበረ ፓትርያርክንም ዘረጋች፡፡ ይህን የረጅም ጊዜ ጉዞ ስንመለከት የቤተ ክርስቲያናችን ዕድገትና ልዕልና በከፍተኛ ጥረትና መሥዋዕትነት የተገኙ መሆናቸውን እንረዳለን፡፡

 

ቤተ ክርስቲያናችን ምን ጊዜም አገልግሎቷን ሳታቋርጥ ለሀገርና ለሕዝብ ጠቃሚ የሆኑ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎቷን ስታበረክት ኖራለች፡፡ ይሁን እንጂ ቤተ ክርስቲያን በዓለም ያለች እንደመሆንዋ በዚህ ጉዞ ውስጥ ሙሉ በሙሉ ከተፅዕኖ ነጻ አልነበረችም፡፡ በእግዚአብሔር ኀይል ያጋጠሟትን ፈተናዎች እየተቋቋመች እዚህ ደርሳለች፡፡

 

ከዚህ ተጨባጭ ሐቅ ስንነሣ ያካሄድናቸው ሢመተ ፕትርክናዎች ሁሉ በተቀመጠው ቀኖናዊ አግባብና በሚፈለገው አቋምና ብቃት ሥሉጣን /የተፋጠኑ/ ሆነው የተጓዙ ነበሩ ብለን በሙሉ ድፍረት መናገር አንችልም፡፡ በርግጥ በሥጋዊውም ሆነ በመንፈሳዊው ዓለም የሰው ልጆች ከመካከላቸው ብልጫ ያለውን ሰው ለከፍተኛ ሓላፊነት ይመርጣሉ፡፡ አንዱን ሰው ከሌላው የበለጠ የሚያደርገው ለመንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት ያለው ቅንና ቆራጥ አስተሳሰብ፣ አቅም ያለው የሥራ አፈጻጸምና የመሳሰለው መልካም ሥራ ሚዛን ሲደፋ እንደሆነም እንገነዘባለን፡፡

 

በዕለታዊ የሥራ አፈጻጸምና በማኅበራዊ አገልግሎት ከሁሉ የበለጠ አስተዋፅኦ በማድረግ የተመሰከረለትን ሰው ለከፍተኛ ሓላፊነት መምረጥ ተመራጩን ለመጥቀም ሳይሆን ሥራውን በማክበር ተገልጋዩን ወገን በበለጠ ለማገልገል ነው፡፡ ይህም የመራጮችን አስተዋይነትና ለትክክለኛ ዓላማ የቆሙ መሆናቸውን ይገልጣል፡፡ የተጓዝንበትም መንገድ መመዘን ያለበት አንዱ ከዚህ መሆን እንደአለበትም እናምናለን፡፡

 

ከዚህ አኳያ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአሁኑ ጊዜ የሚያስፈልጋት ፓትርያርክ ምን ዓይነት አባት ነው የሚለው ጥያቄ የመላው ሕዝበ ክርስቲያን ቢሆንም ይህን ጥያቄ ሊመልስ የሚችለው ምርጫው በራሱ ሳይሆን የምርጫው መደላደል መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ከምርጫው ይልቅ ለቅድመ ምርጫው ቅድሚያ መስጠት የወቅቱ ግዴታ ሊሆን ይገባል፡፡

 

በቅዱስ ሲሄዶስ መሪነት፣ ሊቃውንት ካህናትና ምእመናን በነጻ አሳብና በመንፈሳዊ ትብብር እየተመካከሩ ያለምንም አድልዎና ተፅዕኖ መንፈሳዊ አባታቸውን መምረጥ እንዲችሉና ተመራጩም የቀኖና ቤተ ክርስቲያን ጥያቄ ሳይነሣበት ቤተ ክርስቲያኒቱን በሰላምና በአንድነት እንዲመራ ከምርጫው ይልቅ አሁንም ለምርጫው የሚያስፈልጉ መደላድሎች ቅድሚያ ሊሰጣቸው ይገባል እንላለን፡፡

 

ከእነዚህም መደላድሎች ውስጥ ዋናዎቹ ሦስት ናቸው፡፡ የመጀመሪያውና ዋነኛው የአራተኛውን ፓትርያርክ የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆርዮስን መሰደድና የአምስተኛው ፓትርያርክ የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስን ሢመተ ፕትርክና ተከትሎ የተከሰተው የቤተ ክርስቲያን ለሁለት መከፈል ነው፡፡ ከዚህ አኳያ የተጀመረው ቤተ ክርስቲያንን አንድ የማድረግ ጥረት በእርቀ ሰላም እንዲቋጭ ተገቢውን ርብርብ ማድረግ ቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል፡፡ በሁለቱ አባቶች መካከል ተፈጥሯል የተባለው የቀኖና ቤተ ክርስቲያን ችግር በቤተ ክርስቲያኒቱ በራስዋ ሕጎች፣ ደንቦችና መመሪያዎች መሠረት በመዋቅራዊ አካላቷ ተቋማዊ አሠራር እንዲፈታ መደረግ አለበት፡፡

 

ሁለተኛው የቅድመ ምርጫ መደላድል፤ ሕጎችን፣ ደንቦችንና መመሪያዎችን ማውጣት ወይም ማሻሻል የሚያስፈልግ ከሆነ ተገቢነታቸው በሊቃውንቱ ተሳትፎ እየተጠና ጉዳዩ በቀጥታ በሚመለከተው በቅዱስ ሲኖዶስ እየተወሰነ ተግባራዊ ማድረግ ነው፡፡ ሦስተኛው መደላድል ደግሞ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን ድርጅታዊ አወቃቀር ለማሻሻል የቀረቡና የሚቀርቡ ጥናቶችን በማዳበር የለውጥ ሂደቱን ለመምራት የሚችልና መንፈሳዊነት ሞያዊነት፣ ግልጽነት፣ ተጠያቂነትና ፍትሐዊነት የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የአሠራር መርሕ መሆኑን በተጨባጭ ሊያረጋግጥ የሚችል የቴክኒክ ኮሚቴ በይፋ ማቋቋም ነው፡፡

 

የእነዚህ ሦስት መደላድሎች መቅደም የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተዳደራዊ ነጻነት ከማጎናጸፍና የተለያዩ ሕገ ወጥ ቡድኖችን በዘለቄታዊነት ከአስተዳደራዊ ጣልቃ ገብነት እንዲታቀቡ ከማድረጋቸውም በላይ የተከፈለችውን አሐቲ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ወደ አንድነት ይመራል የሚል ጽኑ እምነት አለን፡፡

 

ስለሆነም ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ምእመናን የቤተ ክርስቲያኒቱ ጉዳይ ያገባናል የምትሉ ምሁራን፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶች፣ የመንፈሳዊ ኮሌጆቻችን ደቀ መዛሙርትና ልዩ ልዩ ማኅበራት ለቤተ ክርስቲያኒቱ እግዚአብሔር ጥሩ መሪ እንዲሰጥ ቅዱስ ሲኖዶስ ያወጀውን የሁለት ሱባኤ ጸሎተ ምኅላ ከመፈጸም ጎን ለጎን ለመደላድሎቹ ስኬት ሁላችንም የድርሻችንን ልንወጣ ይገባል፡፡ ከዚህ አንጻርም የግል ጥቅማቸውን የሚያሳድዱ አንዳንድ ግለሰቦችንና ቡድኖችን ሕገ ወጥ እንቅስቃሴ በንቃት መከታተል ያስፈልጋል፡፡

 

ከዚሁ ጋር ለእነዚህ ሕገ ወጥ አካሄዶች ሽፋን የሚሆኑና በመሠረቱም ተገቢም ትክክለኛም ያልሆኑ መግለጫዎች፣ ቃለ ምልልሶችና ጽሑፎች እንዲታረሙና በቀጣይም እንዲቆጠቡ መደረግ ይኖርበታል እንላለን፡፡

 

በመንፈስ ቅዱስ የሚመራው፣ የመንበረ ሐዋርያት ወራሽና የቤተ ክርስቲያኒቱ የሥልጣን መዋቅር ሁሉ የበላይ አካል የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ ለምርጫው ሳይቸኩል ለቅድመ ምርጫው ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሠራ ጽኑ እምነታችን ነው፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር


ስምዐ ጽድቅ 19ኛ ዓመት ቁጥር 24 2005 ዓ.ም.


አርአያነት ያለው ተግባር

ነሐሴ 3 ቀን 2004 ዓ.ም.


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ


አሁን ያለው የክርስትናው ዓለም ከአለመኖር ወደ መኖር የመጣው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዓለም አቀፍም፤ ሀገር አቀፍም መንፈሳዊ ተቋም በመሆን ስትፈጽመው በኖረችው ሐዋርያዊ አገልግሎት ነው፡፡ ይህን ዓለም አቀፍና ሀገር አቀፍ መንፈሳዊ አገልግሎት ስትፈጽም የኖረችበት ዘመንም በአኃዝ ሲቀመር ከሁለት ሺሕ ዓመታት በላይ አስቆጥሯል፡፡

 

ቤተ ክርስቲያን ከዚህ ዘመን የደረሰችው ያለ ርእይና ዕቅድ በዘፈቀደ በመጓዝ አይደለም፡፡ አባቶቻችን ዘመንን እየቀደሙ እያቀዱና እየተገበሩ፤ አተገባበራቸውንም እግዚአብሔርን አጋዥ አድርገው እየገመገሙ የተዛነፈውንም እያቀኑ ለቤተ ክርስቲያንም ሆነ ለትውልድ የሚሆነውን በጎ ነገር ሁሉ ሠርተው ቀምረው አስተላልፈዋል፡፡

 

ይህን የአባቶቻችን ዓቅዶ መሥራት፣ አፈጻጸሙን ቆም ብሎ ማየትን የሚዘክር ተግባር በጅማ ሀገረ ስብከት እያስተዋልን ነው፡፡ የሀገረ ስብከቱ ራስን የመገምገም ተግባርም ለሎሎችም አህጉረ ስብከት አርአያነት ያለው ነው፡፡

 

በአንዳንድ አህጉረ ስብከት እየደበዘዘ ወይም እየጠፋ ያለውን በዕቅድ መሥራትና አፈጻጸሙን የመገምገም ባህል ከማጎልበት አኳያ የጅማ ሀገረ ስብከት ተግባር ተስፋ ሰጪ ነው፡፡ ሀገረ ስብከቱ በየዓመቱ ጠቅላላ ጉባኤ ማካሔዱ ደግሞ ይበል የሚያሰኝ አካሄድ ነው፡፡

 

በዚህ ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ በሀገረ ስብከቱ ውስጥ የሚገኙ የወረዳ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጆች፣ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች የሰበካ ጉባኤ አባላት፣ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ተወካዮችና የማኅበራት ተወካዮች እንዲሳተፉ ከመደረጉም በላይ የእርስ በርስ የልምድ ልውውጥ መደረጉ በራሰ እጅግ ጠቃሚ መሆኑን እንገነዘባለን፡፡

 

ጠቅላላ ጉባኤው በጨዋነት፣ በመደማመጥና በመከባበር መንፈስ ችግሮችን ነቅሶ በማውጣት በግልጽ ተወያይቶ ለመፍትሔው ሁሉም የድርሻውን እንዲያበረክትና በጠቅላላ ጉባኤው የተላለፉትን ውሳኔዎች አተገባበር መከታተል መቻሉ፣ ያልተተገበሩ ሥራዎች ለምን አልተሠሩም ብሎ መጠየቅ ላይ መደረሱ፣ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስም ሆኑ የሀገረ ስብከቱ ሠራተኞች በሥራቸው ያሉትን ካህናትንም ሆነ ምእመናንን ገንቢ ሂስ በሆደ ሰፊነት መቀበላቸው፤ ሌሎች አህጉረ ስብከት በአርአያነቱ ሊወስዷቸው የሚገቡ በጎ ተግባራት ናቸው እንላለን፡፡

 

በዕቅድ ተመርቶ መሥራትን፣ የዕቅድን አተገባበር መከታተልና የመቆጣጠርን አሠራርን ምን ታቀደ ምን ተሠራ ለምን አልተሠራም ብሎ የዓመቱን የአገልግሎት ጉዞ መለስ ብሎ መመልከትን እንደ ጅማ ሀገረ ስብከት ሁሉ ሌሎችም አህጉረ ስብከት ሊዘምቱበት ይገባል፡፡

 

ዐቅዳ የምትሠራ የሠራችውንም ሥራ ቆም ብላ የምትገመግም ቤተ ክርስቲያን፤ ምንም ጊዜ ቢሆን በየትኛውም ሁኔታ ድል አድራጊ ናት፡፡ ግልጸኝነትና ተጠያቂነትም ተቋማዊ መሠረት እንዲይዙ ያስችላታል፡፡ ለብልሹና አድሏዊ አሠራሮች የተጋለጡ የልማትም ሆነ አስተዳደራዊ ተቋማቶቿን ወደተሻለ ምዕራፍ እንድታሸጋግር ያግዛታል፡፡

 

ከዚህም በላይ ቤተ ክርስቲያናችን ተከታይይዋን ሕዝብ በሰበካ ጉባኤ በማደራጀትና በዚህም ውጤት በተገኘው የገቢ አቅም ጥንካሬ ስብከቷ፣ ትምህርቷ ሕልውናዋ ተጠናክሮ እንዲቀጥል፤ የቤተ ክርስቲያን ችግር ሆነው የኖሩትንም ሆነ የሚሆኑትን አጽራረ ቤተ ክርስቲያን ለመመከት የጅማ ሀገረ ስብከት አርአያነት ለትልቋ ቤተ ክርስቲያናችን ወሳኝ ነው፡፡

 

አጽራረ ቤተ ክርስቲያን ዛሬ ጉዟቸውን ወደ ቤተ ክርስቲያናችን በማድረግና በእኛዋ ቤተ ክርስቲያን ላይ ቀስታቸውን በማነጣጠር ወደ መንጋችን በረት ዘልቀው ለመግብት እያደረጉት ያለውን ሙከራ በሙከራ ደረጀ ለማስቀረት ብሎም እንዳይታሰብ ለማድረግ እንደ ጅማ ሀገረ ስብከት አቅዶ ለመሥራትንና አፈጻጸምን ገምግሞ ለቀጣይ ሥራ መዘጋጀት ይገባል እንላለን፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር


ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 19ኛ ዓመት ቁጥር 22 ከነሐሴ 1-15 ቀን 2004 ዓ.ም.