“ከሁሉ በላይ በምትሆን፤ ሐዋርያት በሰበሰቧት፤ በአንዲት፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም እናምናለን”

ሐምሌ 10 ቀን 2004 ዓ.ም.


ይህ አንቀጸ ሃይማኖት የጉባኤ ቁስጥንጥንያ አንቀጸ ሃይማኖት ነው፡፡ የእውነተኛዋ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መታወቂያ ትእምርትም ነው፡፡ ይህን አጉድሎ መገኘት የቤተ ክርስቲያንን ሕግና ሥርዐት ማፍረስ ብቻ ሳይሆን እምነትንም እንደማጉደል ይቆጠራል፡፡ እንዲህ ዐይነት ማንነታዊ ተክለ ቁመናን ገንዘብ ያደረገ ግለሰብም ሆነ ማኅበር ራሱን የክርሰቶስ አካልና አባል አድርጎ አለመቀበሉን ያሳየናል፡፡ በክርስቶስ ብቻ አምኖ በግለኝነት መኖር በቂ አይደለም፡፡ የክርስቶስ አካል በሆነችው ሐዋርያት በሰበሰቧት፣ በአንዲት፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም አምኖ አባል መሆን ሃይማኖታዊ ግዴታ ነው፡፡

 

ይሁንና ይህን አንቀጸ ሃይማኖት ያለ ዐውዱና ከተሸከመው መልእክት ውጪ በመለጠጥና አዲስ የትርጓሜ ቅርጽ በመስጠት በፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ መናፍቃን ቅላጼና ወዝ “ማኅበራት አያስፈልጉም” የሚል እና ራሱን “ጉባኤ አርድእት ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ” ብሎ የሚጠራ የቤተ ክርስቲያናችን ሕመም የሆነ ቡድን ያለ ቤተ ክርስቲያኒቱ ዕውቅናና ይሁንታ ከሰሞኑ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት መሽጎና የተለያዩ ስብሰባዎችን እያካሄደ እንደሚገኝ ማረጋገጥ ችለናል፡፡

 

ይህን ተከትሎም ከሰሞኑ የመንበረ ፓትርያርኩ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ምንም ዓይነት ስብሰባ ያለ ቤተ ክርስቲያኒቱ ዕውቅና በግቢ ውስጥ እንዳይካሄድ የሚከለክል ደብዳቤም ለሚመለከታቸው አካላት ማሰራጨቱንም ለማወቅ ችለናል፡፡

 

የዚህ የጥፋት ቡድን ዋነኛ ዓላማም ራሱን የቤተ ክርስቲያኒቱ ተቆርቋሪ አድርጎ በመሰየም እና በተቆርቋሪነት ሽፋን ሐዋርያት የሰበሰቧትን አንዲት፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መከፋፈልና የዚሁ ግብር ተዳባይ የሆኑትን እውነተኛ ማኅበራት ህልውና ማክሰምና ጥብዓት ያላቸውን ብፁዓን አበውንና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን መገዳደር ነው፡፡

 

እንዲህ ዐይነቱን የጥፋት ዓላማ ያነገበው እና “ማኅበር አያስፈልግም” እያለ ራሱን ወደ ማኅበርነት ለማሳደግ ዕቅድ ይዞ የሚንሳቀሰው ቡድን የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን ጥቂት የመምሪያ ሓላፊዎችንንና ሠራተኞችን እንዲሁም በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚሠሩ ግለሰቦችን በመሰብሰብ በመመሥረቻ ሰነዱ ላይ ማስፈረሙንም ከሰነዱ ለማወቅ ችለናል፡፡ በአንጻሩ ደግሞ አብዛኞቹ ስብሰባው ላይ በመገኘት የጥፋት ግንባሩ የተደራጀበት መንገድና ዓላማ ለቤተ ክርስቲያን አደጋ እንዳለው አቋማቸውን ገልጠው የወጡ እንዳሉም መገንዘብ ችለናል፡፡

 

የአደራጆቹን ማንነት ስንመለከት ደግሞ ያው መልኩንና ስልቱን በየጊዜው የሚቀያይረው የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ ሰለባ የሆኑ ግለሰቦች መሆናቸውንም አረጋግጠናል፡፡ እየተጓዙበት ያለው የጥፋት መንገድም የተለመደው የተሐድሶ መናፍቃን ስልተ መንገድ ነው፡፡

 

እናም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የሁለት ሺሕ ዓመት ታሪክ ያላት ጥንታዊት ቤተ ክርሰቲያን ትሁን እንጂ መንበሯን ከሊቀ ጵጵስና ወደ ፕትርክና ለማሳደግ አንድ ሺሕ ስድስት መቶ መራራ ዓመታትን ገፍታለች፡፡ በዚህ ማለፏ ደግሞ ሌሎች አኀት አብያተ ክርስቲያናት የደረሱበት የአደረጃጀት ችግር እንዳጋጠማትና ልጆቿን ጊዜው በሚጠይቀው መንገድ ለመሥራት የሚያስችላትን አካሄድ እንዳትጠቀም አድርጓት መቆየቱን በሚገባ እንገነዘባለን፡፡

 

ያለማቋረጥ የተደራረበባት ችግር ሐዋርያዊ ተልእኮዋን እንዳዳከመውና ሊቃውንቷንም ተጠራጣሪና ተከላካይ ብቻ እንዳደረጋቸው ሁሉ የራሷ ሲኖዶስ ሳይኖራት ለረጅም ዓመታት መምጣቷም አሁን ያሉባት ችግሮች የአሁን ብቻ ላለመሆናቸው ጠቋሚ መሆናቸውንም እንረዳለን፡፡

 

እነዚህን ዘመናትን ተሻግረው የመጡ ችግሮች ደግሞ ገና ለጋ ለሆነውና የሃምሳ ዓመታት ተሞክሮ ላለው ቤተ ክህነት ብቻ ትቶ “ብትችል ተወጣው፣ ባትችል የራስህ ጉዳይ” የሚያሰኝ አለመሆኑንም መረዳት ያስፈልጋል፡፡

 

እንኳን የእኛ ቤተ ክርሰቲያን በጠንካራ ሲኖዶስ በመምራትና በሠለጠኑና በተማሩ አማኞቿ የምትታወቀው የግብጽ ቤተ ክርስቲያን በሃያኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ላይ ለተደቀነባት የዓለማዊነትና የፕሮቴስታንት ተሐድሶ ፈተና፣ የርእይ ብዥታና የአስተዳደር ለውጥ ታላቁን አዎንታዊ ድጋፍ ያገኘችው በዘመኑ በነበረው ሊቀ ሐቢብ ጊዮርጊስ አደራጅነት ከተቋቋሙት ማኅበራት እንደነበረም መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

 

ይህ ሊቅ አሁን ባለው የግብጽ ሲኖዶስም ታላቅ ከበሬታ ያለውና እርሱ ባስጀመረው እንቅስቃሴ ቤተ ክርስቲያኒቱ በአሁኗ የኢስላም ሀገር ግብጽ ላይ ታላቅ ሚና እንድትጫወትና ከዓለም ሁሉ የሚመጡባትን ፈተናዎች ተቋቁማ ብቻ ሳይሆን ድል እያደረገች እንድትጓዝ አስችሏታል፡፡

 

በተሳሳተና በፈጠራ መረጃ የተሳከሩት የዚህ የጥፋት ቡድን አደራጆች ሊረዱት የሚገባው ነጥብ፤ ለጠንካራዋ የግብጽ ቤተ ክርስቲያን የማኅበራት አስፈላጊነት ይህን ያህል ከሆነና የሶርያና የሕንድ አብያተ ክርስቲያናት ከመቶ ዓመት በፊት ጀምረው ማኅበራትን በዘመናዊ መንገድ እያቋቋሙ ተጠቃሚ ከሆኑ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንማ እንዴት አያስፈልጓት? አንድ ብቻ አይደለም ገና ብዙ ማኅበራት ያስፈልጓታል፡፡

 

ማኅበራቱም ከሁሉ በላይ በምትሆን ሐዋርያት ለሰበሰቧት፤ ለአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ግብ የሚንቀሳቀሱ፣ ተልእኮአቸውና ዓላማቸው ተለይቶ የሚታወቅ፣ መንፈሳዊ ተግባርን ብቻ የሚፈጽሙ፣ የሚናበቡና በስልት ለአንድ ውጤት የሚተጉ ሊሆኑ እንደሚገባም እናምናለን፡፡

 

ቤተ ክርስቲያኒቱ ዕውቅና ሰጥታቸው የሚንቀሳቀሱ ማኅበራትም አስፈላጊነትም የሚነሣው ከዚሁ ነጥብ መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በምትመራበት ቃለ ዓዋዲ የተገለጡትን የወጣቶች ተግባራት መፈጸም እንደተጠበቀ ሆኖ የቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር ያልሸፈናቸውን ክፍተቶች ለመሙላት ከማገዝ አንጻር አይደለም አንድና ሁለት ማኅበራት የሌሎች ተጨማሪ ማኅበራት አስፈላጊነት ለድርድር የሚቀርብ አለመሆኑን መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡

 

ሐዋርያት የሰበሰቧት አንዲት፣ ቅድስትና ኲላዊት የሆነችው ቤተ ክርስቲያናችን ሦስተኛውን ሺሕ ዘመን እንድትዘልቅ፣ ገዳማትንና አድባራትን የልሂቃን ምንጭ እና የልማት ማእከላት ለማድረግ የሚሠሩ፣ የአብነት ትምህርት ቤቶችንና መንፈሳዊ ኮሌጆቻችን ዘመናዊ ትምህርትን በመጨመር የሚሰጡ የእውቀት ማእከላት ለማድረግ የሚጥሩ፣ ሁለገብ ዕውቀት ያላቸውና ችግር ፈቺ ካህናትን ለማፍራት የሚደረገውን ጥረት የሚያግዙ፣ ዘመናዊ አስተዳደርን በቤተ ክህነቱ በመዘርጋት ተየያዥ ችግሮችን ሁሉ ለመፍታትና ግንዛቤው ያደገና በዕውቀት የበለጸገ ምእመን ማፍራት ግባቸው ያደረጉ በርካታ ማኅበራት ለቤተ ክርሰቲያን ያስፈልጓታል እንላለን፡፡

 

በአንጻሩ ደግሞ “ከሁሉም በላይ በምትሆን፤ ሐዋርያት በሰበሰቧት፤ በአንዲት ቅድስት ቤተ ክርሰቲያን” ሳያምኑ እኲይ ዓላማቸውን ለማስፈጸም ቤተ ክርስቲያኒቷን ጥግ ያደረጉትን እንደ ሰሞኑን የተሐድሶ መናፍቃን መልክ ያሉትን የጥፋት ቡድኖች ደግሞ እንደ ትናንቱ ሁሉ ዛሬም በሃይማኖታዊ ጥብዓት የምንታገላቸው መሆኑን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡

 

ብፁዓን አባቶቻችንም ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን እና ሕገ ቤተ ክርስቲያንን መሠረት አድርገው በፕሮቴስታንታዊ የተሐድሶ ኑፋቄ አራማጆችና እንዲሁም አቀንቃኝ ድርጅቶችና ግለሰቦች ላይ የማያዳግም ውሳኔ ይወስናሉ ብለን እንጠብቃለን፡፡

 

በተለይ ያለ ይሁንታችሁ እና ባለማወቅ የዚሁ የጥፋት ግንባር አባላት ተደርጋችሁ ስማችሁ የተዘረዘረ የቤተ ክርሰቲያናችን ሊቃውንትም ሆነ የመምሪያ ሓላፊዎች ጊዜው ሳይረፍድ ከዚህ የጥፋት ቡድን ራሳችሁን ነጻ በማድረግ ለቤተ ክርስቲያናችሁ ጥብቅና ትቆሙ ዘንድ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

 

ምእመናንም በየሰነዶቻቸው “ከሁሉም በላይ በምትሆን ሐዋርያት በሰበሰቧት፤ በአንዲት፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን” እያሉ ግብራቸው እንደማያምኑ ከገለጠባቸው የጥፋት ቡድኖች ራሳችሁን፣ ቤተሰቦቻችሁንና አጥቢያ ቤተ ክርስቲያናችሁን ትጠብቁ ዘንድ ጊዜ አሁን ነው እንላለን፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን እንደ መንፈሳዊ ተቋምነቱ፤ አባላቱ ደግሞ እንደ አማኝነታቸው ትናንትም ሆነ ዛሬ እንዲሁም ነገ “ከሁሉ በላይ በምትሆን፤ ሐዋርያት በሰበሰቧት በአንዲት፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ማመን ብቻ ሳይሆን መስዋዕትነት እየከፈሉና የሚከፍሉባት ቤታቸው መሆኗንም ጠንቅቀው እንደሚያውቁ መረዳት ያስፈልጋል፡፡

 

ማኅበሩም ሆነ አባላቱ ቤተ ክርስቲያናቸውን በዕውቀታቸውም ሆነ በገንዘባቸው የሚያገለግሉ እንጂ እንደ  ጥፋት ቡድኑ አፈ ቀላጤዎች የቤተ ክርስቲያኒቱን ገንዘብ እየበሉ ቤተ ክርስቲያኒቱን በገዛ ገንዘቧ ለማፍረስ በመናፍቃን ደጅ የሚጠኑ አለመሆናቸውን እነዚሁ አካላት /እውነቱ እየመረራቸውም ቢሆኑ/ ሊያውቁ ይገባል፡፡

 

እንግዲህ ቤተ ክርስቲያን አማኞች እንዲድኑባት ያዘጋጀ እግዚአብሔር ነው፡፡ በክርስቶስ መሠረትነት፣ በመንፈስ ቅዱስ አደራጅቶና ቀድሶ እውነተኛይቱን ቤተ ክርስቲያን ሠርቷታል፤ አቋቁሟታል፡፡፡ ስለዚህ እኛም እንደ ዝግጅት ክፍልም ሆነ እንደ አማኝ ከሁሉም በላይ በምትሆን ሐዋርያት በሰበሰቧት፤ በአንዲት፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም እናምናለን፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ 19ኛ ዓመት ቁጥር 20/2004 ዓ.ም.

20 021

የማኅበረ ቅዱሳን 20ኛ ዓመት ምሥረታ በመከበር ላይ ነው

ግንቦት 2/2004 ዓ.ም.

በ እንዳለ ደምስስ

20 021የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በዓለ ልደትና የማኅበረ ቅዱሳን 20ኛ ዓመት ምሥረታ እሑድ ሚያዚያ 28 ቀን 2004 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ በድምቀት ተከበረ፡፡ “ለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት አብረን እንሥራ በሚል መሪ ቃል በማኅበረ ቅዱሳን ህዝብ ግንኙነት ክፍል የተዘጋጀው መርሐ ግብር በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በጸሎት ተጀምሮ በዝማሬ በስብከተ ወንጌል አገልግሎትና በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ምክር ተካሒዷል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የምዕራብ ትግራይ ሴቲት ሁመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ የአዲስ አበባና የሰሜን ሸዋ ሰላሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ሔኖክ የምዕራብ ወለጋ ጊምቢና አሶሳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የደቡብ ትግራይ ማይጨው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተገኝተዋል፡፡

 

በዕለቱ የተጉኙት ሊቃነ ጳጳሳት ማኅበረ ቅዱሳን አስመልክቶ እንዲህ በማለት ገልጸው ነበር፡፡ “የፈተና ጊዜ ነው ፈተናውን የምናልፈው በእግዚአብሔር ረድኤት ነው እግዚአብሔርን በመከተል ነው፡፡ ሌላ ኀይል የለንም፡፡…. እናንተ እግዚአብሔርን መከተል መርጣችኋልና መጨረሻችሁን እግዚመብሔር ያሳመርላችሁ፡፡ በርቱ፡፡” ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ፡፡/

 

“የዚህ ታላቅ፣ ታሪካዊ፣ ሃይማኖታዊ፣ ሥርዓታዊ፣ መንፈሳዊና ሰዋዊ ማኅበር አካላት ሁሉ ሥራ እየሠራችሁ ነው እዚህ የደረሳችሁት ምርት እያመረታችሁ ያላችሁባቸው ዓመታት ምርታችሁንም እያያችሁና እየተጠቀማችሁበት የምትገኙበት ዕለት ነውና እንኳን አደረሳችሁ” /ብፁዕ አቡነ ሉቃስ/

 

ይህ ማኅበር 20 ዓመታት ሲጓዝ እግዚአብሔር ስለረዳው እግዚአብሔር ከማኅበሩ ጋር ስለሆነ እንደ ኤማሁስ መንገደኞች እግዚአብሔር ስለመራው ነው ዛሬ 20ኛውን ዓመት ለማክበር የበቃው በርቱ፡፡ /ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ/

 

20 037ብፁዕ አባታችን አቡነ ጎርጎርዮስ ሊሞቱ ሲሉ ካስተማሯቸው ተማሪዎቻቸው /ማኅበረ ቅዱሳንን ከመሠረቱት/ መካከል ሁለቱን፣ አንዱን በቀኝ አንዱን በግራ አቅፈው፣ ጸሎት አድርገው የሁለቱን ራስ አጋጭተው በመያዝ” በሉ ልጆቼ መቃብሬ ላይ እናንተ ናችሁ የምታለቅሱት እኔ ለኩሼዋለሁ እናንተ አንድዱት አሏቸው ለአትክልተ ጎርጎርዮስ፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን መሠረታዊ ምንጭና ግንድ ኢየሱስ ክርስቶስ ቢሆንም የማኅበረ ቅዱሳን ግንድ ደግሞ አቡነ ጎርጎርዮስ ናቸው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚገባውን ምግብ እያበላና እያጠጣ እዚህ ያደረሰው ማኅበር ነው፡፡” /ብፁዕ አቡነ ኤልያስ/

 

የማኅበሩ ሰብሳቢ  ሊቀትጉሃን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዮም እንደገለጹት ከ1980 ዓ.ም. ጀምሮ በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ20 022 ካልዕ በዝዋይ ካህናት ማሠልጠኛ ተተኪ ሰባኪያንን ለማፍራት ባደረጉት ጥረት ለመጀመሪያ ጊዜ ከግቢ ጉባኤያት 12 ተማሪዎችን በማሠልጠን ጀመረ፡፡ ዛሬ ይህ ጥረት አድጎ በጅማ፣ በአዋሳ፣ በድሬዳዋ፣ በባሕርዳርና በማይጨው ሥልጠናው ተጠናክሮ በመቀጠል በሺዎች የሚቆጠሩ መምህራንን ማፍራት ተችሏል፡፡ ብለዋል፡፡ አያይዘውም በመላው ዓለም በአገር ውስጥና በውጪ  የማኅበረ ቅዱሳንን እንቅስቃሴ ሲገልጹ ማኅበረ ቅዱሳን 44 ማዕከላት፣ 333 ወረዳ ማዕከላት 181 ግንኙነት ጣቢያዎች 325 የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤያትን በማስተባበርና በመምራት ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡ ከምዕመናን ማኅበረ ቅዱሳንን አስመልክቶ ለተጠየቁ ጥየቄዎች የማኅበሩ ዋና ጸሓፊ ዲ/ን ሙሉጌታ ኃ/ማርያም ምላሽ ሰጥተዋል፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ላይ ከመምህር ቀሲስ እሸቱ ታደሰ ትምህርተ ወንጌል የተሰጠ ሲሆን  የማኅበሩ መዝሙር ክፍል አባላት የአቡነ ጎርጎርዮስ የትምህርት ማዕከል ሕፃናት ተማሪዎች፣ እንዲሁም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ግቢ ጉባኤያት መዘምራን ያሬዳዊ ዝማሬ በየተራ አቅርበዋል፡፡ በመጨረሻም በብፁዕ አቡነ ኤልያስ ቡራኬ የመርሐ ግብሩ ፍፃሜ ሆኗል፡፡

ማሩ አይምረር፤ ወተቱ አይጥቆር

ሚያዚያ 24/2004 ዓ.ም.

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር ተዋቅሮ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኘው ማኅበረ ቅዱሳን በእግዚአብሔር ፈቃድ አገልግሎቱን ከጀመረ እነሆ ሃያ ዓመታት ተቆጠሩ፡፡ ምንም እንኳን ማኅበሩን በራሳቸው ፈቃደኝነት የተሰባሰቡ ኦርቶዶክሳውያን ቢመሠርቱትም የማኅበሩ መሠረታዊ ዓላማ ግን ቤተ ክርስቲያን ተልእኮዋን ለማሳካት በምታከናውናቸው ተግባራት የልጅነት ድርሻውን ለመወጣት በመሆኑ ወደ ቤተ ክርስቲያን መዋቅር በመግባት መተዳደሪያ ደንቡ በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ በተቀመጠለት ተግባርና ሓላፊነት መሠረት አገልግሎቱን እያከናወነ ያለ ማኅበር ነው፡፡ አባላቱም በሀገር ውስጥም ሆነ በውጪ ሀገራት በቤተ ክርስቲያኗ አጥቢያዎች በሚገኙ ሰበካ ጉባኤያት እና ሰንበት ት/ቤቶች ተመዝግበው የሚጠበቅባቸውን ክርስቲያናዊ ግዴታ እየተወጡ ይገኛሉ፡፡ እነዚህ አባላት አብዛኛዎቹ ቤተ ክርስቲያናቸውን በገንዘብ፣ በዕውቀትና በጉልበት ለማገልገል በፈቃዳቸው ቃል የገቡ ቤተ ክርስቲያንና ሀገሪቷ ካሏት ልዩ ልዩ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ተመርቀው ቤተ ክርስቲያናቸውን አገራቸውንና ወገናቸውን በልዩ ልዩ ሙያ እያገለገሉ የሚገኙ ናቸው፡፡

ማኅበሩ በዋናነት አገልግሎቱን የሚያከናውነው በመተዳደሪያ ደንቡ እንደተቀመጠው አባላቱ በገቡት ቃል መሠረት በየወሩ ከሚሰበሰበው ወርኃዊ አስተዋጽኦ ሲሆን ስብከተ ወንጌል ባልተስፋፋባቸው አካባቢዎች ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት ቅዱሳት መካናትና አብነት ት/ቤቶችን በዘላቂነት በልማት ራሳቸውን ለማስቻል የሚሠሩ ኘሮጀክቶችን በጎ አድራጊ የቤተ ክርስቲያኗ ልጆች ከሆኑ ምእመናንና ማኅበራት ጋር በጋራ በመተባበር ይተገብራል፡፡ ማኅበራችን ባለንት ሃያ የአገልግሎት ዓመታት በእግዚአብሔርም በሰውም ሊታዩና ሊዳሰሱ የሚችሉ በጎ አስተዋጽኦዎችን ለሀገርም ሆነ ለቤተ ክርስቲያን እንዳበረከተ ቢያምንም መሥራት ከሚገባው በጣም ጥቂቱን ብቻ እንደሠራና ገና ብዙ እንደሚጠበቅበትም ይገነዘባል፡፡

እስካሁን ያከናወናቸውን መንፈሳዊና ማኅበራዊ ተግባራት ሲያከናውን ሁሉ ነገር አልጋ በአልጋ ሆኖለት ያለችግርና ውጣውረድ አይደለም፡፡ በእርግጥ አገልግሎቱ መንፈሳዊ አገልግሎት ነውና ሁሉ ነገር ምቹ እንዲሆንም አይጠብቅም፡፡ በየጊዜው የሚገጥሙት ችግሮችና ፈተናዎች የተለያየ መልክ ያላቸው ቢሆኑም የፈተናዎቹ ምንጮች ግን ሁለት ናቸው፡፡ የመጀመሪያው ማኅበሩ የቆመለትን ዓላማና የሚያከናውናቸውን በጎ ተግባራት በዓላማ ከመቃወም የሚመነጭ ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ በተሳሳተ መረጃ ምክንያት ወይም ቀርቦ ባለማየት ከሚፈጠር የተዛባ አመለካከት የሚመነጭ ነው፡፡ ከዚህ አንጻር ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የማኅበሩን አገልግሎት እየገጠሙት ካሉት ችግሮች አንዱ በዘመናችን መላው ዓለምን እያወከው ያለው የአክራሪነት አደጋ በአገራችንም ያለውን አሉታዊ ተፅዕኖ ለማሳየት በሚደረጉ ገለጻዎችና የውይይት መድረኮች ግልጽ ባልሆነና በማይወክለው መንገድ የማኅበሩን ስም በመጥቀስ በበጎ አስተዋጽኦው ላይ ጥላ የሚያጠላ ስሜት መፈጠሩ ነው፡፡ ይህ የተዛባ ሥዕል በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በተለያየ መጠንና በተለያየ መንገድ ሲገለጽ መቆየቱና አሁንም እየተገለጸ መሆኑ በአባላቱም ሆነ በሌሎች ምእመናን ዘንድ መደነጋገርን መፍጠሩ አልቀረም፡፡ ምክንያቱም አባላቱም ሆኑ ሌሎች ምእመናን ከከተማ እስከ ገጠር የሚያውቁት የማኅበረ ቅዱሳን ማንነትና ምንነት አሁን እየተባለ ካለው ጋር ፍፁም የማይገናኝ በመሆኑ ነው፡፡

በመግቢያው ላይ እንደተገለጸው ማኅበረ ቅዱሳን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ የመጨረሻ መዋቅር በሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ መተዳደሪያ ደንብ ጸድቆለት፣ የቤተ ክርስቲያኗን መዋቅራዊ አሠራር ተከትሎ እየሠራ ያለ፣ በርቀት ላሉ በሚሠራቸው ሥራዎች ራሱን የሚገልጥ፣ ቀርበው ማየትና ማወቅ ለሚፈልጉ የሚዳሰስና የሚጨበጥ አካል ያለው መንፈሳዊ ማኅበር ነው፡፡ በመተዳደሪያ ደንቡ ላይ ባለው ግልጽ አቋሙ እንዳስቀመጠው በማንኛውም የፖለቲካ እንቅስቃሴ ውስጥ ጣልቃ አይገባም፡፡ ከተሰጠው ዓላማና ተግባር እና ከቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ አገልግሎት አንጻር አቋሙን መግለጽ ሲያስፈልገው የሚገልጽባቸው የራሱ ሚዲያዎች ያሉት ማኅበር ነው፡፡ የአክራሪነት አደጋ በሀገርም ሆነ በቤተ ክርስቲያን ላይ ስለሚያደርሰው ጥፋት፣ መልካም የሆነው የሰዎች እርስ በርስ ተከባብሮ የመኖርን የቆየ አገራዊ እሴት ስለማስቀጠል፣ አገራቸውንና ወገናቸውን በታማኝነትና በቅንነት የሚያገለግሉ ዜጎችን ስለማፍራት እንደ ቤተ ክርስቲያኗ አስተምህሮ ሓላፊነት በተሞላው መንገድ ሲያስተምርና ሲሠራ ኖሯል፤ አሁንም እየሠራ ነው፡፡ ወደፊትም ያስተምራል ይሠራልም፡፡ እንኳን እምነትን ያህል ታላቅ ነገር ይቅርና አንድ ሰው የሚከተለውን ፍልስፍና ሊከተለው የሚችለው ትክክል ነው ብሎ ሲያምን ብቻ ነው፡፡ አንድ ሰው ዛሬ በምድር ላይ ሲኖር የሕይወቴ መርሕ አድርጌ የምጓዝበት ከሞት በኋላም ዘላለማዊ ሕይወት የምወርስበት እምነት /ሃይማኖት/ ትክክል ነው ብሎ ማመኑ በምንም መስፈርት አክራሪነት ሊባል አይችልም፤ ምክንያቱም የእኔ ትክክል ነው ማለት የሌላው ትክክል አይደለም ወይም የእኔ ብቻ መኖር አለበት የሌላው መኖር የለበትም ማለት ሊሆን አይችልምና፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትክክል ናት ብሎ ያምናል፤ እንዴት ትክክል እንደሆነች በንግግርም በግብርም ይገልጣል፤ ይህ ትክክል የሆነው ሁለንተናዊ ማንነቷ ተጠብቆ እንዲኖርም የድርሻውን ይወጣል፡፡ ይህ አስተሳሰብ በምንም መንገድ ሌላውን የማጥፋት መንፈስን ያዘለ አክራሪነት ተብሎ ሊተረጎም አይችልም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ለአገሪቱ ሁለንተናዊ ማንነትና ዕድገት የነበራትን በጎ አስተዋጽኦ መግለጽም ሆነ ዛሬም ይህንን አስተዋጽኦዋን እንድትቀጥል ማድረግ እንደ ክርስቲያንም ሆነ እንደ ዜጋ የሚጠበቅበት ተግባር መሆኑን ማኅበራችን ያምናል፡፡ በመሆኑም ዓለምን የሁከትና የሰቆቃ መናኸሪያ እያደረጋት ያለው አክራሪነት ማኅበራችንን አይገልጠውም፡፡ ይልቁንም ሙስና፣ አለመታመን፣ ወንጀለኝነት፣ በሽታ ፣ ወዘተ  እያተራመሳት ባለችው ዓለም ከተለያዩ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተመርቀው በልዩ ልዩ ሙያ አገራቸውንና ወገናቸውን በቅንነት፣ በታማኝነትና በእውነት የሚያገለግሉ ዜጎችን በማፍራት በራሱ ፈቃድ፣ በራሱ ገንዘብና ጉልበት የበኩሉን እያበረከተ የሚገኝ ማኅበር አገራዊ አስተዋጽኦው በሁሉም ዘንድ በበጎነቱ ጎልቶ ሊበረታታ ሊደገፍ ይገባዋል እንጂ ገጽታውን የሚያጠቁር ማንነቱን የሚያዛባ ሥዕል በመሳልና መደነጋገርን መፍጠር ተገቢ አይመስለንም፡፡

በመጨረሻም ማኅበረ ቅዱሳን ጉድለት ካለበትም ስለ ጉድለቱ በምድራዊም ሆነ በሰማያዊ ሕግጋት ሊጠየቅ የሚችል ሕጋዊ መንፈሳዊ ተቋም እንጂ ምንም የተሠወረ ነገር እንደሌለ አምነን አባላቱም ሆነ ምእመናን ዛሬም እንደ ትላንቱ አገልግሎታችንን አጠናክረን እንድንቀጥል አደራ በማለት በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ማኅበሩን በማይገልጸው ማንነት እየሣልን ያለን አካላት ደግሞ ማሩን ባለማምረር ወተቱን ባለማጥቆር የማኅበሩን አገራዊ አስተዋጽኦ እናበረታታ ዘንድ ማኅበራችን መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡

ሕገ ወጥ ሕግ አስከባሪዎች

ሚያዝያ 24/2004 ዓ.ም.

ከሰሞኑ ለሰሚ የሚያሳፍር፤ አንድ ጉዳይ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ተፈጽሟል፡፡ ጉዳዩን በአንክሮ ለተመለከተው በእጅጉ ያሳስባል፡፡ የሰላ አንደበት ይዘው ያልኾኑትን ነን በማለት የሌላቸውን ሥልጣንና ዕውቀት እንዳላቸው በማስመሰል ደግ አባቶችን የሚያታልሉ፤ ከቤተ ክርስቲያን ጥቅም ይልቅ የራሳቸውን የሚያስቀድሙ ወረበሎች አሉ፡፡ እነዚህ ጆቢራዎች በደጋግ አባቶቻችን አእጋር ሥር እየተርመሰመሱ፤ ዕውቀት መንፈሳዊ ሳያቋርጥ የሚያፈሰውን የእናት ቤተ ክርስቲያን ጡት እየጠቡ አድገውና ጐልምሰው ሊያገለግሉ በተሰበሰቡ ሊቃውንት መካከል እየተሹለከለኩ ተንኮላቸውን ያለድካም ለመፈጸም ሲኳትኑ ይታያሉ፡፡ ከሰሞኑ የሰማነው ግብዝነትን ከአላዋቂነት ጋር አስተባብሮ የያዘ ከንቱ ተግባር፤ እነዚሀን መሰሪዎች አበው በበሰለ አመራራቸው ለይተው በመጠረቅ ከጉያቸው የሚያባርሩበት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንም በዕውቀት ሚዛን መዝነው ማኔ ቴቄል ፋሬስ ብለው ለይተው የሚጥሉበት ሰዓት ከመቼውም ጊዜ በበለጠ መድረሱን የሚያመለክት ነው፡፡ ጊዜ ለሚሰጠው እንጂ ለማይሰጠው ጉዳይ መዘግየት ጉዳቱ ለራስ ነውና፡፡

ጉዳዩ በማኅበረ ቅዱሳን እንቅስቃሴ ጥቅማቸው የተነካ ወይም የሚነካ በመሰላቸው ሰዎች ተቀነባብሮ የነበረ ሴራ ነው፡፡ እነዚህ ግለሰቦች ማኅበሩ በአባቶች መመሪያና ምክር እንዲሁም ጸሎት እየታገዘ የነበረ አገልግሎቱን በተጠናከረ መንገድ ቀጥሎ ባለበት በአሁኑ ጊዜ ከሕግና ትእዛዝ ፍጹም እንደወጣ አድርገው በማቅረብ በአገልግሎቱ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ የሚያመጣ ደብዳቤ ተፈርሞ እንዲበተን ለማድረግ ያደረጉት ከንቱ ሙከራ ነው፡፡ ግለሰቦቹ ይህንን እኩይ፣ በእግዚአብሔርና በሰው ሕግጋት የሚያስጠይቅ ተግባር ለማሳካት ያላደረጉት ጥረት ለአባቶችም ያልቀባጠሩት ማሳመኛ የሚመስል ነገር የለም፡፡ የእኩይ ተግባራቸው መነሻ ያደረጉት ለማኅበሩ እንዲደርስ ያሉትን ማሩን የሚያመር ወተቱን የሚያጠቁር የክስ ደብዳቤ ማርቀቅ ነው፡፡ ለደብዳቤው ርዕሰ ጉዳይነት የመረጡት ዐረፍተ ነገር «ለሕግ የበላይነት ሥልጣን ታዛዥ ሆኖ አለመገኘትን በሚመለከት ይሆናል» የሚል የአማርኛ ሰዋስው ሀሁን ያላለፈ በዚህም የጆቢራዎቹን ማንነት የገለጠ ያልተሟላ ዐረፍተ ነገር ነው፡፡ በዚህ ርዕሰ ጉዳይነት የታሠረው ከንቱ ደብዳቤ በወግ ባልተጻፈ፤ ርዝመታቸው በትልልቅ አናቅጽ ማሠሪያ የተገታ ከሳሽ ዐረፍተ ነገሮች ታጅሏል፡፡ የደብዳቤው ፍሬ ሐሳብ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ፊርማ በጸደቀ ደንብ የተቋቋመው፤ በደንቡም ብቻ ሳይኾን በየዕለቱ በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዐን አበው ተግሣጽ፣ ምክርና መመሪያ እየታገዘ አገልግሎቱን እየፈጸመ ያለው ማኅበረ ቅዱሳን ከቤተ ክርስቲያኗ ማእከላዊ አስተዳደር ቁጥጥር ውጪ ነው፤ በዚህም የሚሰጠውን መመሪያ ለመቀበል ፈቃደኛ አልኾነም የሚል ነው፡፡ ደብዳቤው ይኽንኑ እንቢተኝነት ለመቀልበስ በቤተ ክርስቲያኗ አስተዳደርና በማኅበሩ መካከል «በዕለት፣ በሳምንት፣ በወርና በዓመት ያልተገደበ የመጻጻፍ ተግባር» ሲካሔድ እንደቆየ ያትታል፡፡ ደብዳቤ መጻጻፉ አሁንም «ከመቼውም ጊዜ ጐልቶ የታየበት ወቅት» እንደኾነም ያስረግጣል፡፡ ይህም የማኅበሩን «የበላይ ተጠሪ የሆነውን የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያን» ለወቀሳ የዳረገ መኾኑን ይጠቅስና፤ ማኅበሩ በዚህ ተግባሩ የመምሪያውንም ኾነ የቤተ ክርስቲያን ማእከላዊ አስተዳደር ህልውና እየተፈታተነ እንደኾነ በሬ ወለደ አሉባልታውን ይነዛል፡፡ ለዚህም ማሥረጃ ይጠቅሳል፡፡

መስከረም 12 ቀን 2002 ዓ.ም «ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ በጠቅላይ ቤተክህነት የየመምሪያውና ድርጅቶች ሓላፊዎች እንዲሁም የማኅበሩ ሥራ አመራርና ሥራ አስፈጻሚዎች ወዘተ በተገኙበት የተሰጠውን ባለ 6 ነጥብ «የሥራ አፈጻጸም መመሪያ» ተግባራዊ ለማድረግ ፈቃደኛ አይደለም ይላል፡፡ በማከልም በዚህ የተነሣ ለደረሰው ችግር ማኅበሩን ተጠያቂ በማድረግ፤ ጉዳዩ በቤተ ክርስቲያኗ «ሊኖር የሚገባውን የሥልጣን ተዋረድ የሚሸራርፍ ሆኖ ከመታየቱም በላይ የማእከሉን አስተዳደርና ኃላፊነት ድርሻ የሚጐዳ አካሔድ ያለው» ነው ይልና፤ የማኅበሩ አልታዘዝ ባይነትና ሕጋዊ ያልኾነ እንቅስቃሴ በፍጥነት መታረም እንዳለበት ታምኖበታል ይላል፡፡ ደብዳቤው ይህንን ሁሉ ካለ በኋላ መመሪያ ወደ ማውረድ ይገባል፡፡ «ስለዚህ ይህ ደብዳቤ በደረሳችሁ ከ10 ቀናት ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ ቀደም ሲል መስከረም 12 ቀን 2002 ዓ.ም በምልዓተ ጉባኤ ተወስኖ በተላለፈላችሁ ቃለ ጉባኤ የተቀመጡትን ስድስት ነጥቦች ተግባራዊ እንድታደርጉ እያስገነዘብን በተሰጠው የጊዜ ገደብ ተጠናቆ ካልቀረበ ግን በቤተ ክርስቲያኒቱ መመሪያዎች የተቀመጠውን ድንጋጌ ለማስከበር ሲባል አስተዳደራዊ እርምጃ እንዲወሰድ የሚደረግ መሆኑን እናስታውቃለን» በማለት መመሪያውን በማዥጐድጐድ  ያጠቃልላል፡፡

ጆቢራዎቹ ይህንን ደብዳቤ አርቅቀው በኮምፒውተር ከጨረሱ በኋላ ቀጣይ ከይሲያዊ ተግባራቸው ያደረጉት፤ ደብዳቤው በማደራጃ መምሪያው ሓላፊ ፊርማ ለማኅበሩ እንዲሰጠው ነውና ዓላማው፤ የመምሪያው ሓላፊ ላይ ተጽዕኖ የሚያደርግ ድምጽ ወደ መፈለግ ገቡ፡፡ አወጡ አወረዱ፡፡ ተጽዕኖ ሊፈጥሩ ይችላሉ ወዳሏቸው አባትም ምላሳቸውን አስረዝመው፣ አለባበሳቸውን አሳምረው፣ ያሳምናል ያሉትን ውሸት ቀምረው ቀረቡ፡፡ ቀመራቸው ቅዱስ ፓትርያርኩ ደብዳቤ እንዲጻፍ አዝዘዋልና የመምሪያ ሓላፊው በተዘጋጀው ደብዳቤ እንዲፈርሙ ትእዛዝ ይስጡ የሚል ነበር፡፡ ደጉ አባትም የጆቢራዎቹን ቃል ሰምተው የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊን ጠርተው እንዲህ ዓይነት ደብዳቤ ተዘጋጅቷልና ይፈርሙ ይሏቸዋል፡፡ በጉዳዩ ግራ የተጋቡት የመምሪያው ሓላፊም ደብዳቤውን ሲያነቡ በእሳቸው ስም ሊወጣ የማይችል መኾኑንና ለጉዳዩም እውቅና እንደማይሰጡ መመሪያውን ለሰጧቸው አባት ይገልጻሉ፡፡ በዚህ ሂደት ጆቢራዎቹ ያሰብነው ተሳካ በሚል በመረጡት ሆቴል ፌስታ ያደርጋሉ፡፡ ሁለቱ አባቶች ግን ተመካክረው ጉዳዩ እንዲዘገይ ያደርጋሉ፡፡ በዚህ ሒደት ሌሎች የቤተ ክርስቲያኗ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ይሰሙና ጉዳዩን አዝዘው እንደኾነ ቅዱስ ፓትርያርኩን ይጠይቃሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት ማኅበሩን ዕለት ዕለት እያቀረቡ በመምከር ላይ ያሉት ቅዱስነታቸውም በእሳቸው ስም በተሠራው ወንጀል አዝነው ደብዳቤው ተሠራጭቶ እንደኾነ በአስቸኳይ እንዲሰበሰብ ያዝዛሉ፡፡ የጆቢራዎቹ ከይሲያዊ እንቅስቃሴ በዚህ መንገድ ተኮላሸ፡፡ እውነት የለውምና፡፡

ለመኾኑ ጆቢራዎቹ እነማን ናቸው?

ይህ ከባድ ወንጀል በማኅበሩ ላይ ስለተፈጸመ ሳይኾን ድርጊቱ በቤተ ክህነታችን ውስጥ እየተፈጸመ ስላለውና ወደፊትም ሊፈጸም ከሚችለው ከባድ ጥፋት አንጻር ስለነዚህ ግለሰቦች ወደፊት በዝርዝር እናሳውቃለን፡፡

በመሠረቱ ማኅበረ ቅዱሳን በሁሉም የቤተ ክህነት ደረጃ ሕግ እንዲከበር ይፈልጋል፡፡ ለዚህም ለሕግና ሥርዓት መከበር ቀዳሚ ሓላፊነት ካለባቸው አባቶች ጋር በየጊዜው ይመካከራል፡፡ ቢኾን የሚለውንም በልጅነት ያቀርባል፡፡ ማኅበሩ ይህንን የሚያደርገው ራሱ አባቶች በሰጡት መመሪያ መሠረት ለመሄድ የቻለውን ሁሉ በማድረግ ነው፡፡ በዚህም ጆቢራዎቹ መደረግ አለበት ብለው ያወረዱትን «ትእዛዝ» ቀድሞም ሲያደርገው የነበረው፣ አሁንም እያደረገ ያለው ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ምስክሮቹ ማኅበሩን መመሪያ በመስጠትና እንቅስቃሴውን በመከታተል የሚያሠሩት አባቶች ናቸው፡፡

ማኅበሩ ዘወትር እንደሚለው፤ የቤተ ክርስቲያኗን ማእከላዊ አስተዳደር ጠብቆ በአባቶች መመሪያና ቁጥጥር እንደሚሠራ ምንም ዓይነት ብዥታ ሊኖር አይገባም፡፡ ሕግን አክብሮ በቤተ ክርስቲያኗ ሕግ እንዲከበር በተግባር የሚታገል ነውና፡፡ አሁንም ቤተ ክርስቲያኗ በምትጠይቀው አግባብ ሁሉ ራሱን ለማሳየት ዝግጁ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን ለቤተ ክርስቲያን የተቋቋመ ነውና፡፡ ነገር ግን በማይመለከታቸው እየገቡ አባቶችን በማታለል ለሚሠነዘርበት ጥቃት አበውን ምስክር በማድረግ ምላሹን እየሠጠ ይሄዳል፡፡

ከማኅበሩ አልፎ ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የኾነው የሰሞኑ የማታለል ተግባር በቤተ ክህነታችን እየኾነ ያለው አሳሳቢ H#ኔታ መገለጫ ነው፡፡ አባቶቻችን የነገርን ሁሉ በጐ ገጽታ መመልከትን ሀብት ያደረጉ እንደኾነ ይታወቃል፡፡ ወንጌል ለአነዋወራቸው ሁሉ መመሪያ ነውና፡፡ ነገር ግን ይህንን የዋሕነታቸውን ተጠቅመው በረዘመ ምላሳቸውና ራሳቸውን ለራሳቸው በሚፈጥሩት ከፍ ያለ ማንነታቸው በስማቸውና በፊርማቸው ወንጀል እንዳያሠሯቸው እንሰጋለን፡፡ ለዚህ ተግባራቸውም እውነትን ይዘው ከቆሙ ሊቃውንት ጋር ራሳቸውን አመሳስለው በአበው እግር ሥር መርመስመሳቸውን እናያለን፡፡ ይህ በቤተ ክህነታችን ሥር እያንዣበበ ያለው አደጋ በሁለም ጥረት በኖ ሊጠፋ ያስፈልጋል፡፡ ይህንን ዕውን ለማድረግ በሚደረግ ማንኛውም እንቅስቃሴ ማኅበራችን ንቁ ተሳትፎውን ይቀጥላል፡፡ ለዚህም የአባቶቻችን ምክርና መመሪያ እንደማይለየው ያምናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የቃለ ዓዋዲው ክለሳ በውጭ ያለውን አገልግሎት ያካትት-

ሚያዚያ 1/2004 ዓ.ም.

ሃያኛው መቶ ክፍለ ዘመን በኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን በርካታ ለውጦች የተስተናገዱበት ነበር፡፡ ከለውጦቹ ውስጥ ደግሞ ዋና ዋናዎቹ ሁለት ናቸው ማለት ይቻላል፡፡ የመጀመሪያው ለውጥ በውድ የመጣ ይልቁንም ለውጡ እውን ይኾን ዘንድ ከ0ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ ነገሥታትና ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት የተጋደሉለት ለውጥ ነው፡፡ ይኸውም የቤተ ክርሰቲያኗን አስተዳደር ለ1600 ዘመናት በቅብጥ ቤተ ክርስቲያን ጥላ ሥር እንዲቆይ ያደረገው ሊቃውንት መንበረ ጵጵስናውን ትንሽ ቆይቶም መንበረ ፕትርክናውን ተረክበው ዕውቀት መንፈሳዊ እየመገበች ያሳደገቻቸውን ቤተ ክርስቲያን መምራት የጀመሩበት የለውጥ ምዕራፍ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ቤተ ክርስቲያኗ ለሀገር ለሕዝብ ለምትሰጠው አገልግሎት ዋጋ ይኾናት ዘንድ ከነገሥታት ተሰጥቷት የነበረው ርስት ጉልት ተነጥቆ «ራስሽን ቻይ» የተባለችበት የግድ ለውጥ ነው፡፡

እነዚህ ሁለት ለውጦች በቤተ ክርስቲያኗ ረጅም ታሪክ ሲከሰት ያዩ በወቅቱ የነበሩ አበው፤ ቤተ ክርስቲያኗ በለውጦቹ ግራ ስትጋባ የነበረ ሐዋርያው ተልእኮዋን አጠናክራ በምትቀጥልበት ሁኔታ ላይ መምከርን ያዙ፡፡ የምስክራቸው ነጥቦች የቤተ ክርስቲያኗን አስተዳደር እንዴት ሀገራዊ መልክዕ መስጠት ይቻላል) በገቢዋ ከካህናቷና አገልጋዮቿ የዕለት ጉርስ የዓመት ልብስ አልፎ ሀገርን ትመግብ የነበረች ቤተ ክርስቲያን የነበራት የኢኮኖሚ ምንጭ ከደረቀ ዘንድ፤ አገልግሎቷ በገንዘብ ማጣት እንዳይታጐል ምን ይደረግ) የሚሉ ነበሩ፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ገላጭነትም በርካታ የመፍትሔ አቅጣጫዎች አስቀመጡ፡፡

 

በወቅቱ ከተቀመጡ የመፍትሔ አቅጣጫዎች ውስጥ መሠረታዊው የቤተ ክርስቲያኗን አስተዳደራዊ አንድነት የሚያስጠብቅ፤ ለቤተ ክርስቲያኗ አገልግሎት የሚያስፈልገው ገንዘብም በራሷ ልጆች /ምእመናን/ የሚሸፈንበትን ሁኔታ የሚያረጋግጥ ሕገ ቤተ ክርስቲያን አርቅቆ ሥራ ላይ ማዋል ነበር፡፡ ቃለ ዓዋዲ በመኾኑም ይህ ሕግ በምክረ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ተራቅቆ፤ በትእዛዝ አዋጅ ቁጥር 83/65 ተፈቅዶ፤ ጥቅምት 15 ቀን 1965 ዓ.ም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ ተፈርሞ ሥራ ላይ ዋለ፡፡ ካህናትና ምእመናን በያሉበት በታወቀ መልኩ እየተደራጁ የቤተ ክርስቲያኗን አስተዳደር እንዲመሩ የሚያደርገው ይህ ሕገ ቤተ ክርስቲያን ሥራ ላይ ከዋለበት ጊዜ ጀምሮ ለሕጉ እውን መኾን የተጉት አበው ያሰቡለትን ዓላማ በማስፈጸም ላይ ይገኛል፡፡ በእርግጥ በአፈጻጸሙ ሒደት ከሕጉ የመነጩ ሳይኾን ከአፈጻጸም የሚታዩ ችግሮች መኖራቸው ግልጽ ነው፡፡ የአሁኑ መልእክታችን ዓላማ እሱ ባለመኾኑ ወደዚያ አንገባም፡፡

 

ቃለ ዓዋዲ ሕጋችን በቤተ ክርስቲያኗ ሁሉን አቀፍ እንቅስቃሴ ላይ ያመጣውን አዎንታዊ ለውጥ በምንመለከትበት ጊዜ ጥንካሬውና ብቃቱ ተፈትኖ የተረጋገጠው በሀገር ቤት ባለችዋ ቤተ ክርስቲያን ላይ ብቻ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡

 

ሕጉ ተረቅቆ ሲወጣ ቤተ ክርስቲያናችን በውጪው ዓለም ያልተስፋፋችበት ወቅት በመኾኑ የተቀረጸው በሀገር ቤት ያለችዋን ቤተ ክርስቲያን አስተዳደርና አንድነት እንዲያጠናክር ሆኖ ነበር፡፡ ከአንድም ሦስት ጊዜ የተሻሻለ መሆኑ ቢታመንም በአበው ትጋትና በስዱዳን ልጆቿ ብርታት በውጭው ዓለም እየተስፋፋች ያለችዋን ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን እንቅስቃሴ እንዲያግዝ የሚያስችል አንቀጽ አልተጨመረበት፡፡ ይህም በመሆኑ ቤተ ክርስቲያናችን በውጭው ዓለም በፍጥነት የመስፋፋቷን ያህል አስተዳደራዊ ችግሮቿም እንዲበዙ ሆኗል፡፡ በተለያዩ ክፍላተ ዓለም ለሚቋቋሙ አብያተ ክርስቲያናት ያገለግሉ ዘንድ አባቶች ሲላኩም የሹመት ደብዳቤያቸውን አስይዞ ከመላክ ያለፈ ቤተ ክህነታችን ለአገልጋዩ መመሪያ የሚሆን ወጥ ሰነድ ሲሰጥ አልታየም፡፡ የለምና፡፡ በዚህም የተነሣ በውጭ ያለችው ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ዥንጉርጉር እንዲሆን ሆኗል ማለት ይቻላል፡፡

 

ጠቢቡ «ቦ ጊዜ ለኲሉ» እንዳለው፤ ይህ ችግር ለረጅም ጊዜያት ሲንከባለል ኖሮ፤ በችግሩም ልጆቻቸውን ተከትለው በመሰደድ የሚያገለግሉ አበውም ግራ ሲጋቡ ቢቆዩም ጉዳዩ የቤተ ክርስቲያንኗ ከፍተኛ አመራር አካል /አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ/ አጀንዳ ወደ መሆን የተሸጋገረው ግን በያዝነው ዓመት መጀመሪያ ነበር፡፡ ባለፈው ጥቅምት ወር ፳)፬ ዓ.ም በተካሔደው የአጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ፤ እሱን ተከትሎም የተደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ምልአተ ጉባኤ ተወያይቶ ውሳኔ ካሳለፈባቸው ነጥቦች አንዱ ቃለ ዓዋዲው ወቅታዊውን የአገልግሎት ስፋት ባገናዘበ መልኩ እንዲከለስ፤ በክለሳውም በውጭ ያለችውን ቤተ ክርስቲያን አስተዳደርም ከግንዛቤ ውስጥ የከተተ የሚል ነበር፡፡ ያንን ውሳኔ ተቀብሎ የሚያስፈጽመው አካል /የሰበካ ጉባኤ መምሪያ/ ይህ አንገብጋቢ ጉዳይ በአስቸኳይ ወደ ተግባር እንዲለወጥ በመትጋት ላይ ይገኛል፡፡ እናም መምሪያው በሚያስተባብረው የቃለ ዓዋዲ ክለሳ ሂደት በውጭው ዓለም የምትገኘዋን ቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊ ችግሮች ከግንዛቤ ውስጥ በሚገቡበት ሁኔታ ላይ ቢደረጉ የምንላቸውን ጥቂት ሐሳቦች እንሰነዝራለን፡፡

 

የመጀመሪያው ይሁንታ ለጉዳዩ ቀጥተኛ ባለቤቶች ዕድል በሚሰጥበት ሁኔታ ላይ ያጠነጠነ ነው፡፡ በውጭ ላለችው ቤተ ክርስቲያን የሚመች ሕግ ባለመኖሩ ሲቸገሩ የኖሩትና የሚኖሩት በውጭ ባለችዋ ቤተ ክርስቲያን የሚያገለግሉ ካህናትና ምእመናን ናቸው፡፡ የችግሩን ስፋት የሚያውቁት፣ የመሰላቸውንም መፍትሔ ለመስጠት ሲሞክሩ የኖሩት አሁንም ቢሆን የሚሉት ሐሳብ ያላቸው እነሱ ናቸውና፡፡ በመሆኑም ቃለ ዓዋዲውን በውጭ ላለችዋ ቤተ ክርስቲያን በሚመች መልኩ በመከለሱ ሒደት በውጭው ዓለም የሚኖሩ ካህናትና ምእመናን ጉልህ ድርሻ እንዲኖራቸው ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ለዚህም ሐሳባቸውን በየደረጃው /በአጥቢያ፣ በሀገር በአህጉርና በአህጉራት/ የሚያብላሉበትንና ይሁንታቸውን የሚያዋቅሩበትን መንገድ ዘርግቶ ተግባራዊ ማድረግ ይገባል፡፡ በዚህ ዓይነት የሕግ ረቀቁ ከታች ወደ ላይ እየዳበረ ከመጣ በኋላ አዲስ አበባ ላይ በሚካሔደው መደበኛ አጠቃላይ መንፈሳዊ ሰበካ ጉባኤ ቀርቦ የማጠቃለያ ውይይት ተደርጎበት በቅዱስ ሲኖዶስ ሕግ ሆኖ እንዲወጣ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ይህ መሆኑ አሁን በውጭው ዓለም የሚታየው አስተዳደራዊ ዥንጉርጉርነትና እሱ የወለዳቸውንም በርካታ ችግሮች ይቀርፋል፡፡

 

በውጭ ያለችዋን ቤተ ክርስቲያን አንድነት የሚያጠናክር ማእከላዊ ሕግ ወጥቶ ሥራ ላይ አልዋለም ብንልም፤ በውጭው ዓለም የሚያገለግሉ ካህናትና ምእመናን እንደ የአካባቢያቸው ነባራዊ ሁኔታና ችግሮቻቸው ይዘት መፍትሔ ይሆኑናል ያሏቸውን ሕግጋት እያረቀቁ ተግባር ላይ ሲያውሉ ቆይተዋል፡፡ በመሆኑም በውጭው ዓለም ልዩ ልዩ ይዘት ያላቸው የአብያተ ክርስቲያናት ሕገ ደንቦች አሉ፡፡ ቃለ ዓዋዲውን በመከለስ በተለይ በውጭ ያለችዋን ቤተ ክርስቲያን ችግር የሚያቃልሉ አንቀጾችን በማካተት  ሒደት እነዚህን ሕገ ደንቦች ሰብስቦ ማጥናቱ ተገቢ ነው፡፡ ደንቦቹ ምንም እንኳን በዚያ ያለችዋ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊ ዥንጉርጉርነት መገለጫዎች ሆነው ቢቆዩም አልፎ አልፎ ለክለሳው ግብኣት የሚሆነ ጠቃሚ ሐሳቦች ይኖሯቸዋልና፡፡

 

ከላይ እንዳልነው በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሌለችበት ክፍለ ዓለም የለም ማለት ይቻላል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በስደት ከሄዱ ኢትዮጵያውያን አልፋ፤ በተሰደደችባቸው ሀገራት ጭምርም በጥምቀት ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ እየወለደች ወደ ጉያዋ የምትሰበስባቸው ሕዝቦች እየበዙ ይገኛሉ፡፡ በመሆኑም የቃለ ዓዋዲው ክለሳ ቤተ ክርስቲያኗ እምነት በቀዘቀዘችበት ዓለም ሙቀትና የክርስትና ተስፋ በመሆን የሰበሰበቻቸውን እነዚህን ሕዝቦች በአጥጋቢ ሁኔታ እንድታገለግል የሚያስችላት መሆን ይኖርበታል፡፡

 

ቃለ ዓዋዲውን በውጭ ላለችዋ ቤተ ክርስቲያን በሚመች መልኩ የመከለሱ ውሳኔ የዘገየ ቢሆንም፤ ዛሬ ቤተ ክርስቲያናችን በውጭው ዓለም እያደረገችው ካለው ፈጣን መስፋፋት አንጻር በእጅጉ አስፈላጊና በአስቸኳይ ተግባራዊ መሆን ያለበት ነው፡፡ በመሆኑም ለዚህ ውሳኔ ተግባራዊነት ሁላችንም የበኩላችንን እናድርግ፤ ከዚህም ጋር ዐቅሙና ለጉዳዩ ቅርበት ያለን አካላት ለሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያው ሞያዊ ድጋፍ ልናደርግ ይገባል እንላለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ሀገር ዕርቃኗን እንዳትቀር

መጋቢት 25/2004 ዓ.ም.

ከጥቂት ዓመታት በፊት በታተመ አንድ የተባበሩት መንግሥታት ጥናት፤ ሀገራችን ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. በ2020 ሙሉ በሙሉ ደን አልባ አገር ትኾናለች፡፡ እንደ ጥናቱ ከ40 ዓመታት በፊት የሀገሪቱ 40 በመቶ መሬት በደን ተሸፍኖ ነበር፡፡ ጥናቱ በታተመበት ዓመት ግን ወደ 2.7 በመቶ አሽቆልቁሏል፡፡ ጥናቱ ማስረጃን በመጥቀስ እንዳስቀመጠው ቁጥሩ በሚያስደንቅ ሁኔታ እንዲህ ያሽቆለቆለው በሀገሪቱ 200,000 ሄክታር መሬት በልዩ ልዩ መንገድ ስለሚወድም ነው፡፡ የዚህን ጥናት ግኝት ሌሎች ጥናቶችም ይጋሩታል፡፡ ይህ መረጃ አስደንጋጭ ነው፡፡ በልምላሜና ልምላሜው በሚያመጣው በረከት ለሚኖር እንደኛ ዓይነት ሕዝብ ደግሞ ሁኔታው አስጨናቂ ነው፡፡

ከሀገራችን የተፈጥሮ ደኖች ውስጥ 35 ሺ የሚኾኑት በአድባራትና ገዳማት ዙሪያ ያሉ ደኖች እንደኾኑ ልዩ ልዩ ጥናቶች ያረጋግጣሉ፡፡ እነዚህ ደኖች የሚገኙት በተለይ በሀገሪቱ የሰሜን፣ ሰሜን ምዕራብና መካከለኛው ክፍል እንደመኾናቸው አካባቢው ተፈጥሮ ካደረሰበት መራቆት የተነሣ የችግሩን ስፋትና ግዝፈትም ባያህል የቻሉትን ያህል ሲታደጉት ኖረዋል፤ አሁንም በመታደግ ላይ ይገኛሉ፡፡ ይሁን እንጂ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ እነዚህ ባለውለታ ደኖች በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ አደጋ እንደተቃጣባቸው ወይም እንደደረሰባቸው እናያለን፤ ከሰሞኑ እንኳን በአሰቦት ደብረ ወገግ አቡነ ሳሙኤልና ቅድስት ሥላሴ ገዳም፤ እንዲሁም ደግሞ በዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ደን ላይ ላይ የደረሰውን የእሳት ቃጠሎ ማስታወስ በቂ ነው፡፡ በዚህም እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነታችንም ብቻ ሳይኾን እንደ ኢትዮጵያዊነታችን ደንግጠናል፤ ተጨንቀናልም፡፡ ለምን?

ደኖቻችን የመንፈሳዊ ሀብታችን ምንጮች ናቸው፡፡ ለቅዱሳን አበውና እመው የተመስጧቸው መሠረት፣ የጸሎታቸውም ትኩርት፣ ለዐጽማቸው ማረፊያ ለስውራኑም መናኸሪያ ከተማ ናቸው፡፡ መንፈሳዊ ጥበብ፣ ፍልስፍናና ዕውቀትም በእነሱ በኩል አግኝተናል፤ እናገኛለንም፡፡ ቅዱስ ያሬድ የዜማ ዕውቀትን ያገኘው በዐጸድ መካከል ነው፡፡ የቅኔው ፍልስፍና፣ የአቋቋሙ ጥበብ፣ የመጻሕፍት ምሥጢር የፈላውና በመልክ በመልኩ የተደራጀው በደኖቻችን ሆድ ውስጥ ነው፡፡ ዛሬ ከሀገራችን አልፎ በዓለም ሊቃውንት ቢቀዱና ቢጠኑ የማያልቁት ቅዱሳት ድርሰቶች በአበው ሊቃውንት የተጻፉት ደኖቻችን ቀለምና ብርዕ ኾነው ነው፡፡ ሀገሪቱ በበርካታ ጦርነቶች ያለፈች እንደመኾኗ ደኖቻችን በየዘመኑ በርካታ ቅርሶችን በአደራነት ተቀብለው አኑረዋል፡፡ የተገኙት ተገኝተዋል፡፡ አደራ መቀበላቸውን ያየ ወይም የሰማ ጠፍቶ አደራ በሊታ ላለመኾን ዛሬም ሰንቀዋቸው ይገኛሉ፡፡ የሚመረምር ጠቢብ ትውልድ ቀርቦ እስከሚቀበላቸው ድረስ፡፡ ደኖቻችን ምግቦቻችንም ናቸው፡፡ ይህን ዓለም ንቀው በምናኔ ለሚኖሩ አባቶቻችን በምግብ ምንጭነት ከማገልገላቸውም አንጻር መንፈሳዊ ጥቅማቸው የጎላ ነው፡፡ ደኖቻችን የምድር ልብሶች ናቸው፡፡ በልብስነታቸው በውስጣቸው ላሉ ብርቅዬ የኾኑ እንስሳትና አራዊት መጠጊያ ኾነው ያገለግላሉ፡፡ በመኾኑም በውስጣቸው በያዟቸው ሀብታት ደኖቻችን የተቀደሱ ናቸው፡፡

ደኖቻችን ላቅ ያለ ኢኮኖሚያዊ ጥቅምም አላቸው፡፡ በውስጣቸው ሕዝብ ቢመገባቸው የሚያጠግቡ፤ ቢጠጣቸው የሚያረኩ ፍራፍሬዎች፣ እንስሳትና ማዕድናት የያዙ ናቸው፡፡  እነዚህ ሀብታት በአግባቡ ቢያዙ ከሀገር አልፈው ወደ ዓለም ዐቀፍ ገበያ ቀርበው ለሀገሪቱ የውጭ ምንዛሬ ማምጣት ይችላሉ፡፡ በሌላው ዓለም የሌሉ የእንስሳትም ኾነ የዕጸዋት ዝርያዎችን የያዙ ከመኾናቸው አንጻርም ለቱሪዝም ኢንዱስትሪ ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያደርጋሉ፡፡ ደኖቹ በሚፈጥሩት ልምላሜ አየር የተነሣም ሀገርን የሚያለመልም ጠለ በረከት እንዲወርድ ያደርጋሉ፡፡ ጠለ በረከት ሲወርድ ሕዝብ ጠግቦ ያድራል፤ ኢኮኖሚውም ይገነባል፡፡

ደኖቻችን መድኃኒቶቻችን ናቸው፡፡ በዚህም የሀገርን ኢኮኖሚ ከማሳደግ አኳያ ጥቅማቸው የጎላ ነው፡፡ እንደነ መጽሐፈ መድኃኒት፣ ዕጸ ደብዳቤ፣ መጽሐፈ አዕባን ወዘተ. ዓይነት ደገኛ የነገረ ሕክምና መጻሕፍት በአበው ተጽፈው ለእኛ የደረሱን፤ አባቶቻችን በእነዚህ ደኖች ቤተ ሙከራነት ባደረጉት ምርምር ነው፡፡ የዛሬው ትውልድ ልብ ገዝቶ ከላይ የተጠቀሱትን መጻሕፍት ተጠቅሞ መድኃኒት ልሥራ ብሎ ቢነሣ ንጥረ ነገሮቹን የሚያገኘው ከዚህ ነው፡፡ ሀገር ለራሱ ሕዝብ በራሱ መድኃኒት ፈበረከ ማለት ደግሞ፤ ሕዝቡ ስሙን እንኳን አንብቦ የማይረዳውን መድኃኒት በብዙ ሚልዮን ዶላር ገዝቶ ከማምጣት መዳን ይቻላል ማለት ነው፡፡

ደኖቻችን ከማኅበራዊና ባሕላዊ ጥቅማቸውም አንጻር ድርሻቸው ሰፊ ነው፡፡ የተጣላ የሚታረቀው፣ በሀገርና በወገን በመጣ ችግር ላይ ተወያይቶ መፍትሔ የሚሰጠው፣ ወጣት ኮረዳው በተፈጥሮ የተሰጠውን ችሎታ ፈትሾ የሚያዳብረው በደኖቻችን ነው፡፡

በመኾኑም በምናየውና በምንሰማው መልኩ በተፈጥሮ ደኖቻችን ላይ በቀጥታም ኾነ በተዘዋዋሪ የሚቃጣውና የሚደርሰው አደጋ በሕዝብና በሕዝቡ ማሕደር በኾነው አገር ላይ የሚቃጣና የሚደርስ አደጋ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ስለዚህ ደኖቻችን አልቀው አገር ዕርቃኗን ከመቅረቷ በፊት የሚመለከተን አካላት በሙሉ ርብርብ ልናደርግ ይገባል፡፡

ደን እንደ ኢትዮጵያ ከሰሐራ በታች ላሉ ሀገራት እጅግ አስፈላጊ ነው፡፡ በመኾኑም መንግሥታችን የእነዚህን የተፈጥሮ ደኖች ጥቅም በሚያራምደው የልማትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ውስጥ አብሮ መቀመር ይኖርበታል፡፡ ይህን ስንል ግን እስከ አሁን ምንም ዓይነት ሥራ አልተሠራም በማለት አይደለም፡፡ በእኛ እምነት ቀመሩ አደጋ ለተቃጣባቸውና እየተጎዱ ላሉ ደኖች አስቸኳይ የማዳንና የመጠበቅ እርምጃ በመውሰድ ይጀምራል፡፡ ከዚህም ጋር ሁሉንም ተጠያቂ የሚያደርግ ጠንካራ የደን ሀብት አጠቃቀም ፖሊሲ ማውጣት ያስፈልጋል፡፡ በሌሎች ሀገራት እንደሚታየው ባለ ሀብቶችና ተቋማት የተፈጥሮ ደኖችን በማልማት ተግባርም እንዲሰማሩ በልዩ ልዩ መንገድ ቢያበረታታና መንግሥታዊ ድጋፍም ቢያደርግ መልካም ነው፡፡ ከዚህም ጋር ደኖቹን ለዘመናት ጠብቀው ላቆዩ /በእኛ ረገድ ለገዳማትና አድባራት/ ሙሉ የባለቤትነት መብት ቢሰጥ ለደኖቹ መጠበቅ አስተዋጽዖ ይኖረዋል እንላለን፡፡

ቤተ ክህነታችንም በስሩ በሚገኙ አድባራትና ገዳማት ተጠብቀው ከመንፈሳዊ ጥቅማቸው አልፎ ለሀገር ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ አገልግሎት ሲሰጡ ለቆዩ ደኖች ትኩረት ሊሰጥ ይገባዋል፡፡ ደኖች ለቤተ ክርስቲያኗም ኾነ ለሀገር ሲሰጡ ከኖሩትና እየሰጡ ካሉት መጠነ ሰፊ ጥቅም አንጻር ቤተ ክህነቱ ለደኖች የሚሰጠው ትኩረት የበለጠ መኾን አለበት፡፡ እንደሌላው ሀብቷ ሁሉ ደኖቿ እንደትላንትናው በሁሉም ርብርብ ተጠብቀው ይቆያሉ ብሎ መቀመጥ የዋሕነት ነው፡፡ ዛሬ ሌላ ቀን ከመኾኑ አንጻር እነዚህ ደኖች የሚጠበቁበትን ሥልት መንደፍና ተግባራዊ ማድረግ ይኖርበታል፡፡ ሥልቱም በዋና መሥሪያ ቤቱ ደረጃ በጉዳዩ ላይ የሚሠራ ጠንካራ ተቋም ማቋቋምንም ይጨምራል፡፡

ደኖቻችንን በመጠበቅ ረገድ በባለቤትነት ለዘመናት ተንከባክበው ከጠበቁ ገዳማትና አድባራትም የሚጠበቅ ተግባር አለ፡፡ የመጀመሪያው ተግባር ከአካባቢያቸው የመንግሥት አካላት ጋር በመተባበር የደን ይዞታቸውን ሕግ ባወቀው መንገድ እንዲከበሩ ማድረግ ነው፡፡ ሁለተኛው በማወቅም ይሁን ባለማወቅ ለልዩ ልዩ አገልግሎት ለማዋል በሚል ደኖቹን ከመጨፍጨፍ ተግባር መታቀብ ነው፡፡

ለዘመናት ተጠብቀው የኖሩት ደኖች ተጠብቀው እንዲኖሩ በደኖቹ አካባቢ የሚኖረው ሕዝብም ከፍተኛ ሓላፊነት አለበት፡፡ ደኖቹን ከነሙሉ ሀብታቸው ጠብቀው ያቆዩት ገዳማውያን ወይም የአድባራቱ አለቆችና ካህናት ብቻ አይደሉም፡፡ አሁን በደኖቹ አካባቢ ያለው ሕዝብ አያቶችና ቅድመ አያቶች ጭምር እንጂ፡፡ በመኾኑም ሕዝቡ ከመካከሉ ደኖችን በመቁረጥ ለማገዶና ቦታውን ለልዩ ልዩ አገልግሎቶች የሚያውለውን በተለመደ ባሕሉ ማረምና ችግሩን የሚያቃልልበትን አማራጭ መፍትሔ አብሮ መዘየድ ያስፈልገዋል፡፡ ደኑ ዛሬ ተቆርጦ የዛሬን ችግር ሊያቃልለት ይችላል፡፡ ነገር ግን በደኑ መቆረጥ መሪር ዋጋ የሚከፍሉት ልጆቹና የልጅ ልጆቹ መኾናቸውን ሊረዳ ይገባዋል፡፡
በአጠቃላይ ደኖቻችን /በተለይ በተራቆተው የሀገሪቱ ክፍል የሚገኙት/ ለአካባቢው ሕዝብ ምግብ፣ መጠጥ፣ መድኃኒት፣ የማኅበራዊ እሴቶቹ ማከናወኛ፣ ለሀገርም የኢኮኖሚ ዋልታና የዕውቀት አፍላጋት ስለኾኑ ሁሉም ጥብቅና ሊቆምላቸው ይገባል እንላለን፡፡ ከተለያዩ ሪፖርቶች እንደምንረዳው የቀሩትን ጥቂት ደኖች ማጥፋት ሳይኾን፤ ቆዳው ተልጦ፣ ሥጋው ተበልቶ፣ የገጠጠው አጥንቱም እየተፈረፈረ ያለውን መሬታችንን ዕርቃን የሚሸፍኑ ደኖችን ባስቸኳይ ማልማት አለመጀመር፤ የተጀመሩትን ጥረቶችም ውጤታማ የሚኾኑበትን አግባብ አለማፋጠን የትውልድ ወንጀል ነው፡፡ ስለዚህ መሬታችን ዕርቃኑን እንዳይቀር፤ ዕርቃኑንንም ለልጆቻችን እንዳናስረክብ አደራ አለብን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

በነገር ሁሉ ደስ ልታሰኙ ለጌታ እንደሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እንለምናችኋለን ቆላ.1፥19

ጥር 9/2004 ዓ.ም

በዓላት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎቷን ከምትፈጽምባቸው ሥርዓቶች መካከል እንደ አንዱ ሆነው ይጠቀሳሉ፡፡ በበዓላት ምእመናን ረድኤት በረከት ከማግኘታቸው ባለፈ ቤተ ክርስቲያን የምትሰጣቸውን አገልግሎቶች የሚቀበሉባቸው መንፈሳዊ መድረኮች ናቸው፡፡ በበዓላቱ መምህራን ትምህርተ ወንጌልን ለምእመናን ያደርሳሉ፡፡ በበዓላት አከባበር ሥርዓት ውስጥ ምእመናን በቤታቸው፤ በአካባቢያቸውና በአደባባይ ሁሉም በጋራ በኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነትና ጌትነት፣ ለሰውም ያደረገውን የማዳን ሥራ የሚመሰክሩበት፣ በቤተ ክርስቲያን እምነትና ሥርዓት ላይ ያላቸውን ጽናት ለየትኛውም ወገን ያለሀፍረት የሚገልጹበት የአገልግሎት ዕድል ነው፡፡

ጌታችን “በሰው ፊት የሚመሰክርልኝን እኔም በአባቴ ፊት እመሰክርለታለሁ” /ሉቃ.12፥8/ ያለውን ቃሉን በማክበርና በመጠበቅ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአዋጅና በአደባባይ የምታከብራቸው ማራኪ በዓላት አሏት፡፡ እነዚህ በዓላት በዓይነታቸው ሁሉንም የክርስቲያን ቤተሰብ በየመዓርጉ፣ በየጸጋው እንደየ አቅሙ የሚያሳትፉ በመሆናቸው ደማቅ ናቸው፡፡ በተለይ የጌታችን የመድኀኒትችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሥራ፣ ተአምራትና የማዳን ነገር የሚዘክሩትን በዓላት /በዓለ ልደት፣ ጥምቀት፣ ስቅለት፣ ትንሣኤ፣ መስቀል/ ዐበይት ሆነው ይከበራሉ፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ የበዓላት ቀን ቀመር መሠረትም ብሔራዊ በዓላት እንዲሆኑ በሕግ ተመዝግበው የሚታወቁና ደምቀው የሚከበሩ ናቸው፡፡

እነዚህ ወንጌልን መሠረት ያደረጉ የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ዐበይት በዓላት በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ውስጥና በምእመናን ልብ ከፍ ያለ ቦታ ተሰጥቷቸው መገኘቱ ቤተ ክርስቲያን በታሪኳ ሁሉ ለስብከተ ወንጌል የሰጠችውን የማያቋርጥ ትኩረት ይመሰክራል፡፡ ይህ ለቤተ ክርስቲያን ሕይወቷም አገልግሎቷም ነውና፡፡ እንዲህም ሆኖ እስከዚህ ዘመን ደርሷል፡፡

የዚህ ዘመን የቤተ ክርስቲያን ትውልድም እነዚህን ዐበይት የጌታችንን በዓላት ከጊዜ ጊዜ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት የማክበር ዝንባሌው164149_1457139283455_1682564302_893573_395312_n እያደገ ነው፡፡ ወንጌል በተግባር እየተሰበከ ነው፡፡ ይህም መናፍቃን እኛን ኦርቶዶክሳውያንን ወንጌልን እንደማንሰብክ አድርገው በሚያሙበት ነገር የበለጠ እንዲያፍሩ አገልግሎቱም የበለጠ እንዲሰፋ አድርጓል፡፡ በተለይ በዓለ ጥምቀትን የመሰሉ የአደባባይ በዓላት በየጊዜው እየደመቁ በአከባበር ሥርዓታቸውም ከባህላዊ ይዘታቸው ይልቅ ፍጹም ሃይማኖታዊ መልክ እየያዙ እንዲመጡ እየተደረገ ነው፡፡ ወደፊትም እነዚህ በዓላት በቅዱስ ወንጌል ያለንን እምነት በሰዎች ሁሉ ፊት የምንሰብክባቸው ዓውደ ምሕረቶቻችን ሆነው ደምቀው መከበር እንዳለባቸው ማኅበረ ቅዱሳን የጸና አቋም አለው፡፡ ለዚህም ከልሂቅ እስከ ደቂቅ ሁሉም በቤቱና በአደባባይም ሁሉ በዚህ በረከት በሚገኝበት አገልግሎት መሳተፍ ይጠበቅበታል፡፡ በፍጹም ሰላም፣ ሃይማኖታዊ /መንፈሳዊ/ ፍቅር የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥራና ትምህርቱን፣ ሰውንም የወደደበትን ታላቅ ፍቅር፣ በሰው ሁሉ ፊት በመመስከር በደስታ እንዲያከብሩ ልናነሣሣቸው ይገባል፡፡

ወቅቱን የዋጀ አገልግሎት ከመስጠት አንጻር ደግሞ ከዚህ ቀደም ከነበረው አገልግሎታቸው በበለጠ ትጋት የሚፈለግባቸው ሊቃውንቱና ካህናቱ ናቸው፡፡ ሊቃውንቱና ካህናቱ የበዓላት አገልግሎታችን ሥርዓቱን ጠብቆ በቅልጥፍና እንዲካሔድ ሥምረትም እንዲኖረው ከምእመናን በኩል ያለውን ተነሣሽነት ያገናዘበ ተሳትፎ ልናደርግ ይገባል፡፡ ዞሮ ዞሮ የበዓሉ ማእከል በካህናቱ የሚሰጠው አገልግሎት በመሆኑ በየአጥቢያው ባሉ ማኅበረ ካህናት ምክክር ሊደረግበትም ይገባል፡፡ በበዓላቱ የምንሰጠውን የወንጌል አገልግሎት ሁሉ ምእመናን አውቀው በእምነት አሜን፣ በደስታም እልል እንዲሉ ተርጉመን ምስጢሩን ማስረዳት ይገባናል፡፡ የተቀደሰውን ቅዳሴ፣ የተቆመውን ቁመት፣ የተነበበውን ወንጌል፣ የተሰበከውን ምስባክ፣ የቀረበውን ወረብ ቃሉን ተርጉመን ምስጢሩን ተንትነን ስንነግራቸው የምእመናን ተሳትፎ ይጨምራል፡፡ የአገልግሎቱ ፍቅር የበለጠ ያድርባቸዋል፡፡

164149_1457139483460_1682564302_893577_6995263_nያነሣነውን ታቦት ክብርና ምስጢር፣ የጥምቀተ ባሕሩን ምንነት፣ በዚህም ላይ ቅድስት ወንጌል ያላትን ኀይል ማሳየት ይጠበቅብናል፡፡ ይህ ሲሆን ምእመናን ለካህናት አባቶች ያላቸው የልጅነት መንፈስ ካህናት አባቶችም ለምእመናን ያላቸው የአባትነት መንፈስ ይጨምራል፡፡ በፍቅርና በአገልግሎታችን የበለጠ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንስባቸዋለን፡፡ በዓላትን ለማየት ብቻ የሚታደሙ የውጭና የሀገር ውስጥ ተመልካቾችን ወደ ድኅነት እንጠራለን፡፡

በየበዓላቱ ጉባኤያትን በማዘጋጀት፣ በአደባባይ ዝማሬን በማቅረብ፣ ምእመናንን በመቀስቀስ ታላቅ ድርሻ ያላቸው ሰንበት ትምህርት ቤቶችም የበዓላት አገልግሎቱ ምሰሶና ማገር መሆናቸውን የበለጠ ሊጠብቁ ይገባል፡፡ ቤተ ክርስቲያን በምታከብራቸው የጌታችን ዐበይት በዓላት ያለውን አጠቃላይ የምእመናንን ተሳትፎ የመምራት በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን መሠረትም ቅርጽ የያዘ እንዲሆን የበለጠ መትጋት ይጠበቅባቸዋል፡፡ የዝማሬያችን ጣዕም የአለባበሳችን ድምቀት፣ የዝማሬ ሥርዓታችን ስባት፣ በትሕትናና በፍቅር በመመላለሳችን፣ አንድነታችንና መተሳሰባችን በበዓላቱ ወንጌልን የምንሰብክበትን ክርስቲያናዊ አገልግሎት የበለጠ ያፈካዋል፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሐዋርያቱ በዓለሙ ሁሉ “ምስክሮቼ ትሆናላችሁ” /የሐ.ሥ.1፥9/ ያለውን ቃሉን እያሰብን የበዓላቱን መለከት ልንነፋ ይገባል፡፡ /2ሳሙ.6፥1/ በዓላቱን በማድመቅ ዋጋ እንደሚያገኙ በማመን የሚተጉ፣ እግዚአብሔር በጊዜው ጊዜ ያነሣሣቸውን የየአጥቢያውን ወጣቶችም ለአገልግሎታችን እንደተሰጠን እንደ አንድ ጸጋ ተቀብለን ልንጠቀምባቸው ይገባል፡፡

ምእመናንንም ከበዓላቱ ጋር ተያይዘው የሚዘወተሩ ሌሎች ደባል ሥጋዊ ክንውኖች ሳያዘናጓቸው ሃይማኖታዊ በዓላቱ ለወንጌል አገልግሎት ያላቸውን ድርሻ ማስጠበቅ ይገባቸዋል፡፡ በተለይም ባህላዊ ገጽታ ተላብሰው በበዓላቱ የጎንዮሽ የበቀሉ የሰይጣን ማዘናጊያዎችን ፈር ማስያዝ አለብን፡፡ በዓላችን ቅዱስ ወንጌልን የምንመሰክርበት ነው ካልን የትኛውም ዓይነት የሥጋ /የኀጢአት/ ሥራ ተደባልቆ እንዳይሠለጥንበት ደረጃ በደረጃ ከቤተሰቦቻችን ጀምረን በማስተማር ወደ ፍጹም ክርስቲያናዊ ባህል ማድረስ አለብን፡፡ በዓላቱ ለእግዚአብሔር የተቀደሱ ቀናት ናቸው፡፡ ስለዚህ በስካር፣ በዝሙት፣ በመዳራት፣ በዘፈን፣ በአምልኮ ባዕድ በማመንዘር፣ በጠብ በክርክር ወዘተ ሳይሆን እግዚአብሔርን ደስ በሚያሰኝ ፈሪሐ እግዚአብሔር ባለበት በትሑት መንፈስ በፍቅርና በደስታ በምስጋናም ማክበርን ጠብቀን ሌሎችንም ልናስተምር ይገባል፡፡

በበዓላቱ ሕፃናት፣ አረጋውያን፣ አካል ጉዳተኞችም ያለ ምንም ችግር በበዓላቱ እንዲሳተፉ ምቹ ሁኔታ መፍጠርም ይገባል፡፡ በዓላት በባህሪያቸው ደስ ብሎን የምናመሰግንባቸው ናቸው፡፡ በመሆኑም ምስኪኖችን በማጽናናት በመደገፍ ከበዓሉ የክርስቲያን ወገን የሚገኘውን ደስታ ሁሉ ተሳታፊ ሆነው አምላካችንን እንዲያመሰግኑ እናግዛቸው፡፡ በዓሉን የክርስቲያን ወገን የሚያገኘውን ደስታ ሁሉ ተሳታፊ ሆነው አምላካችንን እንዲያመሰግኑ እናግዛቸው፡፡ በዓሉን የክርስቲያን ወገን የሚያገኘውን ደስታ ሁሉ ተሳታፊ ሆነው አምላካችንን እንዲያመሰግኑ እናግዛቸው፡፡ በዓሉን ለመድኀኒታችን ክብር ለእኛም በረከት እንዲሆን ብለን እስከ ጠበቅነው ድረስ ታናናሾችን መቀበልና ማክበር እርሱን መቀበልና ማክበር መሆኑን የነገረንን ቃሉን ማሰብ ተገቢ ይሆናል፡፡ በአጠቃላይ ሐዋርያው “በነገር ሁሉ ደስ ልታሰኙ ለጌታ እንደሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እንለምናችኋለን” እንዳለው በዓላት ማንንም ሳናሳዝን ለሁሉም ወገን ሐሴትን የምንሞላበት እንዲሆኑ ያስፈልጋል፡፡ ይህንንም ስናደርግ ጌታችን ደስ በሚሰኝበት የወንጌል ቃሉን በማሰብ፣ በመመስከር ሊሆን ይገባል እንላለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡- ሐመር 19ኛ ዓመት ቁጥር 8 ታኅሣሥ 2004 ዓ.ም

በግቢ ጉባኤያት ለሚሰጥ የአብነት ትምህርት አገልግሎት ትኩረት እንስጥ

ኅዳር 28/2004 ዓ.ም.


የአብነት ትምህርት የቤተ ክርስቲያናችን አገልግሎትና የአገልግሎት  ሥርዓት መሠረት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ይህ የአብነት ትምህርት የኢትዮጵያ የትምህርት ታሪክ መሠረትና አንድ አካል ሆኖ ቆይቷል፡፡ የዘመናዊ ትምህርት በሀገራችን መስፋፋቱን ተከትሎ ግን የአብነት ትምህርት ቤቶች ሚና ቤተ ክርስቲያን ለምትፈልገው አገልግሎት በሚያበረክተው ድርሻ ብቻ ተወስኖ እንዲቀር ሆኗል፡፡ ከዚያም አልፎ ቤተ ክርስቲያን የነበራትን የመተዳደሪያ ሀብት ንብረት ማጣቷ በአብነት ትምህርት ቤቶች ጥንካሬ ከዚያም አልፎ በህልውናቸው ላይ ፈተኝ ሁኔታዎች ጋርጧል፡፡

ከእነዚህ ተጽዕኖዎች በላይ ግን አሳሳቢ የሆነው ከአብነት ትምህርት የሚወጡ ደቀመዛሙርት ዘመናዊውን ትምህርት የሚቀስሙበት አሠራር አለመኖሩ ነው፡፡ በአንጻሩ ደግሞ ዘመናዊውን ትምህርት የሚከታተሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች ለአብነት ትምህርቱ ባዕድ ሲሆኑ መታየታቸው ነው፡፡ እነዚህ ሁለት ዓለማት በአንዲት ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ውስጥ እየታዩ መምጣታቸው በአገልግሎት አሰጣጡ እና አቀባበሉ አለመግባባት፣ በቤተ ክርስቲያን የአገልግሎት አሰጣጥ ሥርዓት አንድነት ላይ ፈተና የማስከተል አዝማሚያ እንዲታይ አድርጓል፡፡ በተጨማሪም ቤተ ክርስቲያን በዘመኑ ልትጠቀምበት የሚገባውን የአሠራር፣ የአደረጃጀት፣ የአመራርና የአስተዳደር ዘይቤ ከዘመናዊው የትምህርት ሥርዓት እንዳትወስድ አድርጓታል፡፡

እነዚህ መራራቆች በቤተ ክርስቲያን አገልጋዮችና አገልግሎቱን በሚቀበሉ ምእመናን መካከል ያለው ግንኙነት ላይ ችግሮች ሊያስከትሉ የሚችሉ ናቸው፡፡ በመጀመሪያ በአገልግሎት አሰጣጡ የሚያስፈልገውን ሥነልቦናዊ አንድነት ያሳጣል፡፡ ከዚያ ውጭ አንዱ የትምሀርት ምንጭ ለሌላው ያለው አተያይ የተዛባ እንዲሆን ያደርጋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንንም ዘመናዊ የሚባለው ዓለም ያመጣውን ዕሴት ሁሉ በጭፍን የምትቃወም፣ የምትጸየፍም ያስመስላል፡፡ በአንጻሩ ዘመናዊ የሚባለው ዓለም የቤተ ክርስቲያን የሆነውን ሁሉ ኋላቀር አድርጎ የማሰቡ አዝማሚያ ይታያል፡፡ ስለዚህ ይህንን የአመለካከት መራራቅ አጥፍቶ ቀጣይነት ያለው መፍትሔ ለማምጣት እንዲሁም በዘመናዊው ትምህርት ደቀመዛሙርትና በአብነት ትምህርት ደቀመዛሙርት መካከል በአገልግሎት አሰጣጥና አቀባበል ያለውን የመንፈስ አንድነት ለማምጣት ርእይ ይዞ፣ የሚጠይቀ ውን ስልታዊ ዕቅድ አውጥቶ ወደ ሥራ መግባት ተገቢ ነው፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ይህንን ርእይ እውን ለማድረግ የሚቻለው በሁለቱም ዓይነት ትምህርት ምንጭ በሆኑ ትምህርት ቤቶች ማለትም በአብነት ትምህርት ቤቶችና በዘመናዊው ትምህርት ተቋማት /ዩኒቨርሲቲዎችና ኮሌጆች/ ላይ ቢሠራ እንደሆነ ያምናል፡፡ ስለዚህ እነዚህ ሁለት ተቋማት ማኅበሩ ያለውን የአገልግሎት ርእይ እውን ለማድረግ የመረጣቸው ስልታዊ ተቋማት ናቸው፡፡

በመሆኑም የአብነት ትምህርት የሚሰጥባቸው ጉባኤያት በተለያዩ ምክንያቶች እንዳይፈቱ ለማድረግ ምእመናንን በማስተባበር ለትምህርት ቤቶቹ እድገት፣ ለመምህራኑ እና ለደቀመዛሙርቱ ኑሮ ከሚያደርገው ቁሳዊ ድጋፍ በተጨማሪ በጉባኤያቱ ከሚሰጠው መንፈሳዊ የአገልግሎት ትምህርት ጎን ለጎን የዘመናዊው ትምህርት ዕሴቶች ከሆኑት የአስተዳደር፣ የአመራር እና የሙያ ሥልጠናዎችን እንዲያገኙ እየተጋ ነው፡፡

ዘመናዊው የትምህርት ሥርዓት ተግባራዊ በሚደረግባቸው ኮሌጆችና ዩኒቨርሲቲዎች ላሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች ደግሞ ባቅራቢያቸው ባሉ አብያተ ክርስቲያናት ሰብስቦ የተለያዩ መንፈሳዊ አገልግሎቶችን በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡ ከእነዚህ አገልግሎቶች አንዱ ደግሞ የአብነት ትምህርት ነው፡፡ ተማሪዎች ዘመናዊ ትምህርት በሚከታተሉባቸው የትምህርት ተቋማት ውስጥ ሆነው  ከአብነት ትምህርት ጉባኤያት ጋር እንዲተዋወቁ፤ ከዚያም ባለፈ በጉባኤያቱ ተምረው አስመስክረው እንዲወጡ፤ የዲቁናና የቅስና መዓርገ ክህነት እንዲቀበሉ ለማድረግ ጥረት እያደረገ ነው፡፡ የአብነት ትምህርት ጣዕምና መዓዛ ስበት ቀላል ባለመሆኑ በትምህርት ቆይታቸው ጊዜ ብቻ ሳይሆን ከትምህርት ገበታም ውጭ በሥራ ላይ እያሉ የመከታተል፣ የማስፋት፣ የማሳደግ ፍላጎት እንዲያድርባቸው ያደርጋል፡፡

የዚህ ተግባር ዋነኛ ግቦችም አስቀድመን የጠቀስነውን የአብነት ትምህርቱን ክብርና አስፈላጊነት ከኮሌጅና ዩኒቨርሲቲዎች የሚወጡ፣ ሀገሪቱ ወደፊት ከፍተኛ ሓላፊነት የምትሰጣቸው፣ የሀገራ ችን ዕድገት ፖሊሲ አውጪና አስፈጻሚ ልሂቃን እንዲያውቁት፣ እንዲወዱት፣ እንዲያከብሩት፣ እንዲያገለግሉበትና እንዲገለገሉበ ትም ማድረግ ነው፡፡ የኮሌጅና የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እነዚህን ጉባኤያት ባወቋቸው ቁጥር እንደሚወዷቸው ይታመናል፡፡ ከወደዷቸው ደግሞ ይንከባከቧቸዋል፤ ያበለጽጓቸዋል፡፡ ስለዚህ የአብነት ትምህርቱን ህልውና ከማስጠበቅም አንጻር ታላቅ ሚና ይኖራቸዋል፡፡ ከዚያ ባለፈ ግን የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት በሀገሪቱ የተለያዩ ሓላፊነትን፣ የሙያ ስምሪትንም ይዘው ከሚሠሩ ልሂቃን ጋር በአንዲት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት አሰጣጥ ሥርዓት ውስጥ ተግባብተው የማየት ርእይ እውን ይሆናል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ይህ ርእይ የሁሉም የቤተ ክርስቲያን ወገን ርእይ መሆኑንም ያምናል፡፡ ከዚህ እምነት በመነሣትም የሁሉም ወገን ርእይ እውን እንዲሆን ደረጃ በደረጃ በሚፈጸሙ ተግባራት ውስጥ ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣ ይሻል፡፡ የሁሉም አካላት ድርሻ የሚመነጨው ደግሞ ካለን አቅም ነው፡፡ ለዚህች ሀገር ዕድገት በጎ ሐሳብ ያላቸው መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የአብነት ትምህርት የቤተ ክርስቲያን የአገልግሎት ዕውቀት ብቻ ሳይሆን የሀገሪቱ መንፈሳዊ ቅርሶች አንዱ አካል፣ ለማኅበረሰቦች የአኗኗር ባህልና ዕሴት አስተዋጽኦ የነበረውና ያለው የትምህርት ሥርዓት በመሆኑና የሀገራችን የትምህርት ታሪክ መሠረት በመ ሆኑ በሚመለከቷቸው ሓላፊነቶች በኩል ሊያደርጓቸው የሚገቡ አስተዋጽኦዎችን ማበርከት ይገባቸዋል፡፡

ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን አካላት ድርሻ ግን መተኪያ የሌለው ነው፡፡ በዚህ ረገድ ምእመናንና የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ከፍተኛ ባለደርሻ ናቸው፡፡ በየደረጃው ያሉ የቤተ ክርስቲያናችን አስተዳደር አካላት በተሰጣቸው የሓላፊነት ደረጃ ልክ የወደፊቱን የቤተ ክርስቲያናችንን የአገልግሎት አካሔድ የተሻለ ለማደረግና ከፈተና ለመጠበቅ መጣር ይገባቸዋል፡፡ በኮሌጆችና ዩኒቨርሲቲዎች የሚገኙ ተማሪዎች የአብነት ትምህርትን ቀስመው እንዲወጡ ከማነሣሣት ጀምሮ አገልግሎቱን እንዲያገኙ ምቹ ሁኔታ መፍጠር፣ ልባዊ ድጋፍም መስጠት ይጠበቅባቸዋል፡፡

ምእመናን ደግሞ የአብነት ተማሪዎችንና ትምህርት ቤቶችን መምህራንና ደቀመዛሙርቱን ለመደገፍ እንዲቻል ማኅበረ ቅዱሳን የሚያደርገውን ጥረት በገንዘባቸው፣ በጉልበትና በዕውቀታቸው  ለመደገፍ ያለመሰልቸት መንቀሳቀስ ይመበቅባቸዋል፡፡ በኮሌጅና ዩኒቨርሲቲዎች የሚገኙ ተማሪዎችም የአብነት ትምህርት መርኀ ግብሮችን በተጓዳኝ መከታተል እንዲችሉ ማበረታታት ይገባቸዋል፡፡ ወደኮሌጆች ከመግባታቸውም በፊት ተማሪዎች በየትውልድ አካባ ቢያቸው አብነት ትምህርትን ለመከታተል ዝንባሌ እንዲያድር ባቸው ማድረግ ይገባቸዋል፡፡

በየደረጃው ያሉ የማኅበራችን ማዕከላትም ምቹ ሁኔታ ተፈጥሮ የአብነት ትምህርት ለመከታተል ለተዘጋጁ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ስልታዊ በሆነ መንገድ ተምረው ዘመናዊውን ትምህርት በብቃት የተከታተሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች በአገልጋይነትም ሲሳተፉ ለማየት የያዝነውን ርእይ እውን እንዲሆን ሊተጉ ይገባል፡፡ ለዚህም ተማሪዎቹን ማነሣሣት፣ መምህራንና የትምህርት ቦታውን ማዘጋጀት፣ ከሚከታተሉት ዘመናዊ ትምህርት ጋር የተጣጣመ መርኀ ግብር መንደፍ፣ የተማሩትን ትምህርት ደረጃ እንዲያውቁ በአጥቢያቸው ባሉ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎቶች እንዲሳተፉ ማድረግ የየጊዜውን ሂደት መገምገም እና የመሳሰሉት ተግባራት ሁሉ ይጠበቁብናል፡፡

በአጠቃላይ በዚህ ረገድ ለተያዘው ርእይ እውን መሆን ድርሻ አለኝ የሚሉ አካላት ሁሉ ባላቸው አቅምና ችሎታ ሚና እንዲጫወቱ ማኅበራችን ይጠይቃል፡፡ ሁሉም ወገን የቤተ ክርስቲያን  አገልጋዮቿ በሁሉም ነገር አቅማቸው የጎለበተ ሆነው በአንድ ሐሳብ በአንድ ልብ ለቤተክርስቲያንና ለሀገር ተስፋ እንዲሆኑ መጣር ይገባል፡፡

 

ምንጭ፡- ሐመር 19ኛ ዓመት ቁ.6 ጥቅምት 2004 ዓ.ም

ስለሚያስቷችሁ ሰዎች ይህንን ጽፌላችኋለሁ 1ኛ ዮሐ.2፥27

ቀን፡ ነሐሴ 6/2003 ዓ.ም.

ሐሰት አንናገርም፤ እውነትንም አንደብቅም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ የተነጣጠረው የ”ተሐድሶ” ዘመቻ ውጥን ብዙ ዐሥርት ዓመታት ያለፉት ቢሆንም ከ1992 ዓ.ም. የካቲቲ ወር ጀምሮ ግን ማኅበረ ቅዱሳን ተጨባጭ በሆኑ የምስልና የድምፅ ማስረጃዎች ዘመቻውን በማጋለጥ የቤተ ክርስቲያናችን ቅዱስ ሲኖዶስ ውግዘት ማስተላለፉ ይታወቃል፡፡ ከዚያ በኋላ “ተሐድሶ” ስልቶቹን በመቀያየር ሃይማኖታችንን ለማጥፋትና በሌላ ፕሮቴስታንታዊ አስተምህሮ ለመተካት የሚያደርገውን ሩጫ ቀጥሏል፡፡ በመሆኑም ማኅበረ ቅዱሳን ካለፈው ነሐሴ 2002 ዓ.ም ጀምሮ ይፋዊ የሆነ ከእነዚህ ሴረኞች ቤተ ክርስቲያንን የመጠበቅ እንቅቃሴ ጀምሯል፡፡ የሐመር መጽሔት ልዩ እትምን በማዘጋጀት የተጀመረውን አገልግሎት በሌሎችም በኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያዎች ከካህናቱ ከሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶችና ከሕዝበ ክርስቲያኑ ጋር ፊት ለፊት በተደረጉ ውይይቶች በመታገዝ ሰፊ ግንዛቤ መፍጠር ተችሏል፡፡ በዚህም የ”ተሐድሶ”ን ምንነት፣ መሠረት፣ ግብና ዓላማ፣ ስልት፣ ያለበትን ደረጃ፣ በሌሎች እኅት አብያተ ክርስቲያናት ፈጥሮት የነበረውን ቀውስና መዘዝ፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ዒላማ ለማድረግ በይፋ በተለያዩ የኅትመት ውጤቶች እያደረገ ያለውን እንቅስቃሴ ለማብራራት ጥረት ተደርጓል፡፡

ይህንን በማድረግ ሂደት ውስጥ ይህንን ቤተ ክርስቲያንን የመጠበቁን እንቅስቃሴ ለማጨናገፍ የተሐድሶ” አራማጅ ቡድኖች የተለያዩ ስያሜዎችንና አካላትን በመጠቀምና “የተሐድሶ” እንደ ሸረሪት ድር ሠርቶት የነበረውን የጥፋት መረብ ሳይበጣጠስና በውስጥም በውጭም የሠራው መሠረት ሳይናድ ለማስቀጠል ባለ በሌለ ኃይሉ እየተንቀሳቀሰ ነው፡፡ ይሁን እንጂ እያንዳንዱ ምእመን በእግዚአብሔር ረድኤት የዕለት ከዕለት ተግባሩን ከማከናወን ጋር የቤተ ክርስቲያንን ጉዳይ በንቃት መከታተልና መቆጣጠር በሚችልበት ደረጃ ላይ እየደረሰ ነው፡፡

 

በዚህ ተስፋ እየቆረጠ ያለው የ”ተሐድሶ” መሠሪ ኃይል ከቅርብ ጊዜ ጀምሮ በተለያዩ ተላላኪዎቹ በኩል ሊነዛ የፈለገው ተራ ማታለያ “ተሐድሶ የለም”፣ “ተሐድሶ” የሚል ነገርን የፈጠረው ማኅበረ ቅዱሳን ነው” የሚለውን አባባል ነው፡፡ ይህን አካሔድ ተራ ማታለያ ነው የምንለው የ”ተሐድሶ” መኖር ሊስተባበልበት የማይችልበት ደረጃ ላይ መሆኑን ራሱ “ተሐድሶ” አለመረዳቱ ነው፡፡ መሣሪያ አድርጎ የተጠቀመባቸው መነኮሳትና ካህናት በየፕሮቴስታንቱ አዳራሽ ሲጨፍሩ እየታየ፣ የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ የቅዱሳንን ገድልና ድርሳን እንደልቦለድ የሚቆጥሩ ጋዜጣና መጻሕፈት እንዳሸን እየተሠራጩ፣ ዕቅድና ስልት አውጥቶ እየሠራ መሆኑን ራሱ “ተሐድሶ” በሚዲያዎቹ እየገለጸልን፣ ቤተ ክርስቲያን ከዕለት ዕለት እየተፈተነችበት፣ ከጥቅመኞችና የሥነ ምግባር ችግር ካለባቸው በቤተ ክርስቲያንኒቱ አስተዳደር ውስጥ ካሉ አንዳንድ ግለሰቦች ጋር በማበር አያወካት እየታየ “ተሐድሶ የለም” የሚለው ልፈፋ የዘገየ ስልትና ተራ ማታለያ ከመሆን አይዘልም፡፡

 

ከዚሁ ጋር ተያይዞ የታየው ሌላው አስደንጋጭ ነገር በቤተ ክርስቲያናችን አስተዳደር ውስጥ ያሉ አንዳንድ አካላት “ተሐድሶ የለም” በሚለው ሐሳብ ተስማምተው በአንዳንድ መድረኮች በቀጥታና በተዘዋዋሪ ይህንኑ አስተሳሰብ የሚያጸና አስተያየት ሲሰጡ መታየታቸው ነው፡፡ እነዚህ አካላት ቅዱስ ሲኖዶስ ከዚህ ቀደም የችግሩን መኖር አምኖ፣ አሳማኝ ማስረጃዎች ቀርበውለት ውግዘት ማስተላለፉን ዘንግተውና በተለያዩ ዘመቻዎች “ተሐድሶ” ቤተ ክርስቲያን ላይ የሚወረውረውን ፍላጻ ከምንም በመቁጠር የ”ተሐድሶ” ሴራ ታይቶ እንዳልታየ፣ ተሰምቶ እንዳልተሰማ ሆኖ በምእመናን እንዲታለፍ በመቀስቀሳቸው ብዙዎችን ከማሳዘናቸውም ባለፈ ከፍተኛ ጥርጣሬ አሳድሯል፡፡ እነዚሁ ወገኖች ሐሰትን ሊነግሩን እውነትንም ሊደብቁን የፈለጉበት ምክንያት በሂደት ግልጽ እየሆነ የሚሔድ ሆኖ ሁሉም አካላት ግን የእነዚህን ወገኖችና የመሰሎቻቸውን አቋም እንዲያጤኑ ማኅበረቅዱሳን መልእክት ለማስተላለፍ ተገዷል፡፡

 

“ተሐድሶ የለም” እያሉ በተለያየ መንገድ ለሚነዙት ማደናገሪያዎች ማብራሪያና ማስተባበያ እንዲሰጥባቸው የአዲስ አበባ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ያነሡትን ጥያቄ ተገቢ መሆኑን ማኅበራችንም ያምንበታል፡፡ እነዚሁ አካላት በዚሁ አቋማቸው የመጽናት ፍላጎት ካላቸው ግን “ተሐድሶ” በአደባባይ በሠራቸው ፀረ ቤተ ክርስቲያን ዐዋጆች፣ ስድቦች፣ በጋዜጣ፣ በመጽሔትና በመጻሕፍት በሚያሠራጫቸው የተደበላለቁ ፕሮቴስታንታዊ አስተምህሮዎች ይስማማሉ ወደሚል መደምደሚያ ሊያደርስ ይችላል፡፡ ይህ ከሆነ ደግሞ በተሐድሶ ላይ የምናደርገውን ዘመቻ የሚያደናቅፍ ለየትኛውም ፀረ ቤተ ክርስቲያን እንቅስቃሴ በር የሚከፍት በመሆኑ ለቤተ ክርስቲያን ህልውና፣ አስተምህሮ እና ሥርዐት በመቆም ችግሩን በመቅረፍ ሂደት ማኅበረ ቅዱሳን እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ የድርሻውን ለመወጣት ያለውን መንፈሳዊ ቅናት ምን ጊዜም ይገልጻል፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን ማኅበር ሆኖ በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ የተቋቋመበት ዓላማ ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ነው፡፡ የአገልግሎቱ መገለጫ ደግሞ ስብከተ ወንጌልን ማስፋፋት የቤተክርስቲያኒቱን ዶግማና ቀኖና መጠበቅና ማስጠበቅ እንዲሁም ከአጽራረ ቤተ ክርስቲያን መጠበቅ ካልቻልን የምናገለግላት ቤተ ክርስቲያን ወዴት አለች? በመሆኑም የአዲስ አበባ ሰንበት ትምህርት ቤቶች የያዙትን “ብረሳሽ ቀኜ ትርሳኝ” የሚለው የቅዱሳን መሓላ በእኛና በሁሉም አማኝ ክርስቲያን ደም ውስጥ ማደሩ የግድ ነው፡፡ ስለዚህ በዚሁ ረገድ እውነት እንዲደበቅ፣ ሐሰትም እንዲነገር የሚወዱ አጽራረ ቤተ ክርስቲያንን መገሰጽ፣ መምከርና ከአባቶች ጋር በመመካከር አስፈላጊውን ክርስቲያናዊ እርምጃ በየደረጃው መውሰድ የሁሉም የክርስቲያን ወገን ግዴታ ነው፡፡ በመሆኑም “ተሐድሶ” በሚል ሥያሜ በአጽራረ ቤተ ክርስቲያን የረጅም ጊዜ ዕቅድና ስልት የቤተ ክርስቲያንን ህልውና ለመፈታተን፣ አስተምህሮዋንና ሥርዐቷን ለመናድ በከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ እና ዕቅድ እየተደረገ ያለው ዘመቻ ያለና ተጨባጭ እውነታ እንጂ ማኅበረ ቅዱሳን ከመሬት ተነሥቶ ያወራው አለመሆኑን ማኅበረ ቅዱሳን በአጽንኦት ያሳስባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡- ሐመር 19ኛ ዓመት ቁ.3 ሐምሌ 2003 ዓ.ም

መምሪያው ለቤተክርስቲያን ወጣቶች ተፈጠረ እንጂ ወጣቶች ለመምሪያው አልተፈጠሩም

/ምንጭ፦ሐመር መጽሔት 19ኛ ዓመት ቁጥር 2 ሰኔ 2003ዓ.ም/

ለመንጋው ምሳሌ ሁኑ እንጂ ማኅበሮቻችሁን በኃይል አትግዙ 1ጴጥ. 5፣ 3

ቤተክርስቲያናችን በዚህ ዘመን ትኩረት ሰጥታ ልትፈጽማቸው ከሚገባት ተግባራት አንዱ፤ ወጣቶች በቤተክርስቲያን ውስጥ ያላቸውን አገልግሎት ከመቼውም ጊዜ በላይ ማሳደግና ቤተ ክርስቲያን የምትሰጠውን መንፈሳዊ አገልግሎት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረግ ነው፡፡ ይህ ጉዳይ ትኩረት እንዲሰጠው የሚያደርጉ በርካታ ነገሮች አሉ፡፡ በዋናነት ግን ሥጋዊው ዓለም በቤተክርስቲያን ወጣቶች ሃይማኖታዊ ሕይወትና  መንፈሳዊ አኗኗር ላይ እያሳደረ ያለው ጫና ነው፡፡ ከመረጃ ቴክኖሎጂ ማደግና እርሱን ተከትሎ እየሰፋና እያደገ የመጣው የሉላዊነትና ዘመናዊነት አሉታዊ ገጽታ ባመጣው ግፊት፤ ወጣቶች ባሏቸው ክርስቲያናዊ ኑሮና እሴቶች ላይ ፈተና ደቅኖባቸዋል፡፡

በርካቶች የዚህ ጫና ሰለባ በመሆን ለብ ወዳለ አኗኗር ራሳቸውን እየለወጡ ነው፡፡ ሌሎች ደግሞ ዓለሙን መስለው፣ የክርስትናን አስተምህሮ ሸርሽረው፣ ሕግና ትእዛዛቱን አሽቀንጥረው ጥለው ለሥጋ ፍላጎታቸው በሚመች መንገድ በራሳቸው ማስተዋል ባቋቋሟቸው ቤተ እምነቶች ወስጥ ታቅፈዋል፡፡ ይህም ሆኖ እንኳን ትክክለኛ ሃይማኖታቸውን ከልብ የተረዱና የዘመኑ የክህደት ማዕበል የተረዳቸው በርካታ ወጣቶች ያንን በመቋቋም የራሳቸውን ሕይወት ለመጠበቅና የቤተክርስቲያንን አስተምህሮ፣ ትውፊትና ሥርዐት እንደተከበረ ለቀጣይ ትውልድ ለማሸጋገር እየተጉ ነው፡፡ ለዚህም በየአጥቢያው ባሉ ሰንበት ትምህርት ቤቶችና ማኅበራት ገብተው ሕግና ሥርዐት በሚፈቅደው መንገድ አገልግሎት እየሰጡና እየተቀበሉ ይገኛሉ፡፡ ይሁንና ጊዜው ከሚጠይቀው ምላሽና ጥረት አንጻር እየተጫወቱ ያሉት ሚና በቂ አይደለም፡፡ ይሄ ውስንነት የተፈጠረው ግን በወጣቶቹ የተሳትፎ ፍላጎት ማጣት ሳይሆን፡፡ የወጣቶቹን ዘርፈ ብዙ የአገልግሎት ፍላጎት በቅልጥፍናና በበቂ ሁኔታ እምነትም በሚጣልበት አመራር ማስኬድ አለመቻሉ ነው፡፡

እንደሚታወቀው ቤተክርስቲያን የአጠቃላዩን የወጣቶች አገልግሎት አሰጣጥና አቀባበል፣ ውጤታማ ለማድረግ እንዲቻል የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ አቋቁማ ለዓመታት እየሠራች ቆይታለች፡፡ መምሪያው በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ ቢቆይም አሁን እያደገ ላለው የወጣቶች ተሳትፎ በሚመጥን ደረጃ ግን ራሱን ለውጧል ማለት አይቻልም፡፡ የዚህ ችግር መሠረታዊ ምክንያት ደግሞ የቤተክርስቲያን ወጣቶችን የጊዜውን በጎ ፍላጎት ከግምት ያስገባ፣ ወጣቶች ያሉባቸውን ችግሮች ተደራሽ ያደረገ፣ ርእይና ተልእኮውን በውል ያስቀመጠ፣ መነሻና መድረሻው የሚታወቅ ስልታዊ ዕቅድ ያለው፣ ወጣቶች ለሀገርም ለቤተ ክርስቲያንም ዕድገት አዎንታዊ ሚና እንዲጫወቱ ለማድረግ የሚያስችል አቅም የያዘ አለመሆኑ ነው፡፡ መምሪ ያው አፈጻጸሙ እንዲዳከምና የሚፈለ ገውን አስተዋጽኦ እንዳያበረክት ያደረ ገው የመምሪያው ሓላፊ በራሳቸው አቅምና ፍላጎት ብቻ አሠራሩን ለመገደብ ስለሚጥሩ ነው፡፡

በዚህም ምክንያት አሁን ባለው በራሱ በማደራጃው አቅም ልክ ብቻ የወጣቶች ተሳትፎ እንዲወሰን ሲጥር እንጂ ከእርሱ እየቀደመ ስላለው የሰን በት ትምህርት ቤቶችና የማኅበራት እንቅስቃሴ በሚመጥን ሁኔታ የራሱን አቅምና የአገልግሎት አሰጣጥ ሲያሳ ድግ አይታይም፡፡ እንደውም እንዲቀጭጭ የሚፈልግ አካል በውስጡ መኖሩ ጉዳዩን የበለጠ አሳሳቢ አድርጎ ታል፡፡ ይህም ሁኔታ ማኅበረ ቅዱሳን እያደረገ ባለው ዘርፈ ብዙ እንቅስቃሴ ላይ እየፈጠረ ያለው መሰናክል ለዚህ እንደ ማስረጃ የሚጠቀስ ነው፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በመላው ሀገሪቱ ያለውን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የመስፋፋት ዕድል ተጠቅሞ በየተቋማቱ ያሉትን የቤተክርስቲያን ወጣቶች በሃይማኖታዊ ሕይወታቸው ጸንተው እንዲቀጥሉና አስቀድመን የጠቀስናቸውን የዓለምን ወጣቶች እየተፈታተኑ ካሉ ዘመን አመጣሽ ጾሮች እንዲድኑ ለማ ድረግ እየሠራ ነው፡፡ ለዚህም የቤተ ክርስቲያናችንን ትምህርት አሰጣጥ መሠረት ያደረገ ሥርዐተ ትምህርት ቀርጾ መዋቅሩንም አጠናክሮ እየተራመደ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በአጥቢ ያዎችና በሰንበት ትምህርት ቤቶች ባለው ተሳትፎ አባላቱ ጉልህ ሚና እን ዲጫወቱ እያደረገም ነው፡፡ ስብከተ ወንጌል እንዳይዳከም ገዳማትና አድባ ራት እንዳይዘጉ፣ የአብነት ትምህርት ቤቶች እንዳይበተኑ፣ የቤተክርስቲያን ክብሯ፣ ታሪኳ እንዳይደፈር ለማድረግ በስፋት እየተንቀሳቀሰ ነው፡፡ ሌሎችም ሰንበት ትምህርት ቤቶችና ማኅበራት በዚህ ደረጃ አገልግሎት መስጠት በሚ ያስችል ደረጃ ላይ ደርሰው ቤተክርስቲያናችን ከጌታዋ የተሰጣትን መንፈሳዊ አደራ በብቃት እንድትወጣ ጠንክሮ እየሠራ ነው፡፡

ይህ በእንዲህ እያለ ነው በተደጋጋሚ እየተሰማ እንዳለው የማደራጃ መመሪያው ሓላፊ በተለያዩ ሚዲያዎች ተገቢ ያልሆነና አንድ መምሪያ አገልግሎት በሚሰጣቸው አካላት ላይ ሊፈጽመው የማይገባ ስም ማጥፋት እየፈጸሙ የሚገኙት፡፡ ነገሩን የበለጠ አስገራሚ የሚያደርገው ደግሞ አገልግሎት እንዲሰጣቸው ታስቦ በሥሩ እየተንቀሳቀሱ በመላው ሀገሪቱ ላሉ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ይህ ነው የሚባል ተጨባጭ ለውጥ የሚያመጣ ሥራ አለመሠራቱ እየተነገረ ባለበት ሁኔታ ውስጥ መሆኑ ነው፡፡ በቤተክርስቲያኒቱ ውስጥ አገልግሎት የሚሰጡና የሚቀበሉ ወጣቶች ለሀገርም ለቤተክርስቲያንም ፍሬ ያለው ተግባር እንዲፈጽሙ ለማበረታታት ፈቃደኝነት የማይታይበት መምሪያ የአገልግሎት ፍጥነት እየተጠየቀ ባለበት በዚህ ዘመን የማኅበረ ቅዱሳንን አገልግሎት ለማዘግየት መነሣቱ ከላይ ለጠቀስነው ለመምሪያው የመምራት ብቃት ማነስ ዐቢይ ምስክር ነው፡፡

የዚህም መነሻ ጌታችን ሰንበት ለሰው ተፈጠረ እንጂ ሰው ለሰንበት አልተፈጠረም እንዳለው ሥርዐት፣ መዋቅር፣ ሕግ፣ ደንብ፣ መመሪያ ለክርስቲያኖች ሰላም ለሰውም በጎ ፈቃድ የሚዘጋጅ መሆኑን በውል ያለማጤን ችግር ነው፡፡ በተለይ የመምሪያው ሓላፊ ችግር ሰንበት ትምህርት ቤቶችና ማኅበራት ለመምሪያው የተፈጠሩ እንጂ መምሪያው ለእነርሱ የተፈጠረ አድርጎ ያለማሰብ እንደሆነም እናስባለን፡፡ ይህ ደግሞ ሰንበት ትምህርት ቤቶችንና ማኅበራትን የማገልገል ሳይሆን የመግዛት፤ በግለሰቦች ፈቃድም ላይ ተደግፈው እንዲሔዱ የማስገደድ ዝንባሌን አስከትሏል፡፡ ይህ እየተባባሰ ከመጣ ደግሞ ወጣቶች ዓለሙ እያስከተለባቸው ባለው ጫና ላይ የታከለ የውስጥ ፈተና ስለሚሆን ጥያቄ ማስከተሉ አይቀርም፡፡ ስለዚህ በሰንበት ትምህርት ቤቶችና በማኅበራት ታቅፈው የጊዜያቸውን ፈተና ለመቋቋም ለተሰለፉ፣ የሚሰጣቸውን ሃይማኖታዊ አገልግሎት በጉጉት ለሚጠባበቁ ወጣቶች ቤተክርስቲያን የአገልግሎት አሰጣጧን በመፈተሽ ማስተካከያ ማድረግ አለባት እንላለን፡፡ ለዚህ ስምረት ደግሞ የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናትን ተሞክሮ ማየቱ ጠቃሚ ይሆናል፡፡

ለዚህም ችግሮችን ከመቅረፍና ዘመኑን የዋጀ ተአማኒነት ያለው አሠራር ከመዘርጋት አንጻር የሚመለከታቸው የቤተ ክህነቱ አካላት ገንቢ የሆነ ሚና ሊጫወቱ ይገባል፡፡ በተለይ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶችና ማኅበራት የልባቸውን የሚያደርስ፣ ቤተክርስቲያንን የሚፈለገው ስኬታማ ደረጃ ላይ ለማድረስ የምናደርገውን እልህ አስጨራሽ እንቅስቃሴ የሚያፋጥን አመራር ማደራጃ መምሪያችን እንዲሰጥ ግፊት ማድረግ አለብን፡፡

ከምንም በላይ ሰንበት ትምህርት ቤቶችና ማኅበራት የማደራጃ መምሪያው አገልግሎት ተቀባዮች በመሆናቸው አገልግሎት የሚሰጣቸውን መምሪያ በሚያቅደው ዕቅድ ላይ የመወያየት፣ በአጠቃላይ የአፈጻጸም ሪፖርቱን የመገምገም፣ በየጊዜው ያለበትን አቅም እየፈተሹ በደካማ አሠራሩ የማሻሻያ አስተያየት የመስጠት ወዘተ ሓላፊነትና ክርስቲያናዊ ግዴታችንን መወጣት ይኖርባቸዋል፡፡ ቃለዐዋዲው ባስቀመጠው መሠረት የተሰጠውን ሓላፊነት ለመወጣት በየደረጃው ላሉ የማደራጃ መምሪያው ተወካዮች በቂ ድጋፍ እየሰጠ ተግባሩን ለማከናወን የሔደበትን ርቀት መለካት ይገባናል፡፡ ተጠሪ ለሆነለት አካል ብቻ ሳይሆን አገልግሎት ሊሰጣቸው ቃልኪዳን ለተቀበለባቸው ሰንበት ትምህርት ቤቶችና ማኅበራትም ሪፖርት እያቀረበ የሚመዘንበትን አሠራር ለማስፈን መጣር ይኖርብናል፡፡

በዋናነትም ቅዱስ ሲኖዶስ ለማደራጃ መምሪያው ሊቀ ጳጳስ በመመደብ የጀመረውን ትኩረት የመስጠት እንቅስቃሴ፤ በቀጣይም የአገልግሎት ተቀባዮቹን የማኅበራትና የሰንበት ትምህርት ቤቶች አስተያየትና በጎ ፍላጎት ተቀብሎ እየመከረ ማስተካከያ በመስጠት ሊያጠናክረው እንደሚገባ ማሳሰብ ይጠበቅብናል፡፡ ቤተክርስቲያን ይህን ታላቅ ሓላፊነት የጣለችበትን መምሪያ በብቁ የሰው ኃይል፣ የበጀትና የማቴሪያል አቅምም እንዲኖረው ትኩረት ሊሰጠው ይገባል እንላለን፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ከእነዚህ ማኅበራትና ሰንበት ትምህርት ቤቶች ተነጥላ የምትሰጠው አገልግሎት፤ ለአገልግሎቱ የምታስተባብረው ቅድሚያ የሚሰጠው አካል አለ ብለን እናምንም፡፡ ወጣቶች የዛሬዋ ቤተክርስቲያን ብርቱ አገልጋዮች ለነገው ትውልድ ከማስረከብ አንጻርም የቤተክርስቲያን ማኅበረሰቡ እምብርት ናቸው፡፡

ስለዚህ ማኅበራትና ሰንበት ትምህርት ቤቶች የሚኖረንን ድርሻ ከማስጠበቅ አንጻር በየደረጃው ካለው የቤተክርስቲያን አስተዳደር አካላት ጋር በመምከር በዚሁ ረገድ ያለንን የጸና አቋም ለብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ባገኘነው አጋጣሚ ሁሉ በመግለጽ አገልግሎታችንን የሚያስተባብረው መምሪያ የአገልግሎት ተቀባዮችን በጎ ፍላጎት መሠረት ያደረገ ያአሠራር ማሻሻያ እንዲደረግበት፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቤተክርስቲያኒቱ የተለያዩ መምሪያ ሓላፊዎችና ሠራተኞች በየደረጃው ባሉ መዋቅሮች ያሉ የቤተክርስቲያኒቱ አስተዳደር አካላት ሰንበት ትምህርት ቤት ማደራጃ መመሪያ እንቅስቃሴ አሁን እያደገ የመጣውን የቤተክርስቲያኒቱ ወጣቶች የአገልግሎት ተሳትፎን የሚመጥን አለመሆኑንና ከዚህም አልፎ በመምሪያው በሓላፊነት ያሉ አንዳንድ ግለሰቦች አፍራሽ በሆነ እንቅስቃሴዎች ውስጥ በመግባታቸው ያለውን አሠራር መሸከም የማይቻልበት ደራጃ ላይ እየተደረሰ መሆኑን እንዲረዱን ይፈለጋል፡፡

ብዙ ማኅበራትና ሰንበት ትምህርት ቤቶችንም እያደራጀ ውጤታማ ሥራ ከመሥራት ይልቅ፤ የተደራጁትም እንዲፈርሱ፣ ለግለሰቦች ግልጽና ስውር ፍላጎት እንዲንበረከኩ፣ ከእግዚአብሔር ይልቅ ለሰው እንዲታዘዙ ለማድረግ ጥረት እየተ ደረገ ነው፡፡ በዚሁ ሁሉ ምክንያት ወጣቶች ጊዜው ካስከተለባቸው ፈተና በላይ በአሠራርና በቢሮክራሲ ስም ከፈተናው ለማምለጥ ከተሰበሰቡበት መርከብ ለማስወጣት የሚደረገው ጥረት አሳሳቢ ሆኖ ይገኛል፡፡ ስለዚህ አስቀድመን የጠቀስናቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደር አካላት በማደራጃ መምሪያው ስም የሚንቀሳቀሱ አንዳንድ ግለሰቦችን ሩጫ በመግታት ረገድ ከፍተኛ ሚና ሊጫወቱ ይገባል፡፡ የቤተክህነት ወገኖች የሚያከብሯቸውን፣ ተከብረውም እንዲኖሩ የሚፈልጉ ወጣት የሰንበት ትምህርት ቤትና ማኅበራት አባላትን ጥያቄዎችና ስሜቶች በአግባቡ እያጤኑ መሔድ የቤተክህነቱ ወገኖች ሁሉ ሓላፊነት ነው፡፡ ይህም በዘላቂነት ከምእመናን ጋር ቤተክህነቱ ለሚያደርገው ግንኙነትና አጠቃላይ አገልግሎት አሰጣጥ ስኬት ወሳኝ መሆኑን ተረድተው የመምሪያው አሠራሮች እንዲስተካከሉ መምከር አለባቸው እንላለን፡፡ ቤተክርስቲያንን ለትውልድ ለማስረከብ ተረካቢውን ትውልድ ትኩረት ሰጥቶ በአግባቡ  መቅረጽና ማደራጀት ተገቢ ነውና፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን አባላቱ በጋራም፣ በተናጠልም በየአጥቢያ ሰንበት ትምህርት ቤቱና በመዋቅራቸው የሚያደርጓቸውን አገልግሎቶች በስፋት የማስቀጠሉን ጥረት አጠናክረው እንደሚሔዱ እየገለጸ ለአጠቃላዩ የወጣቶች የአገልግሎት ተሳትፎ ማደግና ችግሮችን ለመቅረፍ በሚደረገው ጥረት ከመቼውም ጊዜ በላይ አሁን በትጋት እየተንቀሳሱ መሆኑን መግለጽ ይፈልጋል፡፡