ዘመነ ክረምት ክፍል አራት

ጳጕሜን ፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! በክፍል ሦስት ዝግጅታችን ከነሐሴ ፲ እስከ ፳፰ ቀን (ከማኅበር እስከ አብርሃም) ድረስ ያለው የዘመነ ክረምት ክፍለ ጊዜ ‹‹ዕጕለ ቋዓት፣ ደሰያት፣ ዓይነ ኲሉ›› እንደሚባል፤ ይኸውም የሰውን ልጅ ጨምሮ የሰማይ አዕዋፍ፣ የምድር አራዊትና እንስሳት ሳይቀሩ እግዚአብሔርን ተስፋ አድርገው በደስታ መኖራቸው፤ በተጨማሪም በዝናም አማካይነት በዙሪያቸው ያለው የውሃ መጠን ከፍ ሲልላቸው ደሴቶች ኹሉ በልምላሜ ማሸብረቃቸው የሚነገርበት ክፍለ ክረምት እንደ ኾነ በማስታዎስ ከሕይወታችን ጋር የሚጣጣም ትምህርት አቅርበን ነበር፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን ደግሞ ቀጣዩን ክፍል ይዘን ቀርበናል፡፡

ከዚያ በፊት ግን ባለፈው ከጠቀስናቸው ትምህርቶች መካከል ‹‹ለነፍሳችሁ በምትበሉት ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ …›› /ሉቃ.፲፪፥፳፪-፴፩/ የሚለው ኃይለ ቃል እንደ እንስሳት ሳትሠሩ እግዚአብሔር ምግብ እንዲሰጣችሁ ለምኑት ማለት ነውን? የሚል ጥያቄ ሊያስነሣ ስለሚችል በመጠኑ ክለሳ አድርገንበት እንለፍ፤ ኃይለ ቃሉን ለማብራራት ያህል የሰው ልጆች ከእንስሳት ከምንለይባቸው ባሕርያት አንደኛው ሠርተን መብላት መቻላችን ነው፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትም የታታሪነትንና የሠርቶ ማደርን ጥቅም እንጂ ሳይሠሩ ተቀምጦ መብላትን አላስተማሩንም፡፡ በብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች የሰው ልጅ እጁ ከሥራ መለየት እንደማይገባው ተጠቅሷል፡፡ ለምሳሌም ጥቂቶቹን እንመልከት፤

በኦሪት ዘፍጥረት እንደ ተጻፈው አባታችን አዳም ከሳተ በኋላ በምድር ጥሮ፣ ግሮ እንዲኖር ተፈርዶበታል፡፡ ይህንንም ‹‹… የምድርንም ቡቃያ ትበላለህ፡፡ ወደ ወጣህበት መሬት እስክትመለስ ድረስ በፊትህ ወዝ እንጀራን ትበላለህ›› ከሚለው ኃይለ ቃል ለመረዳት እንችላለን /ዘፍ.፫፥፲፰-፲፱/፡፡ በተመሳሳይ መልኩ እግዚአብሔር አማላክ አዳምን ከዔደን ገነት ያስወጣው የተገኘባትን መሬት ያርስ ዘንድ ነው /ዘፍ.፫፥፳፫/፡፡ ይህም የሰው ልጅ ሠራቶ አዳሪ ፍጥረት መኾኑን የሚያመላክት ነው፡፡

ጠቢቡ ሰሎሞንም ‹‹አንተ ታካች! እስከ መቼ ትተኛለህ? ከእንቅልፍህስ መቼ ትነሣለህ? ጥቂት ትተኛለህ፤ ጥቂት ታንቀላፋለህ፡፡ ትተኛም ዘንድ ጥቂት እጅህን ታጥፋለህ፡፡ እንግዲህ ድህነትህ እንደ ወንበዴ፣ ችጋርህም ሰይፍ እንደ ታጠቀ ሰው ይመጣብሃል›› በማለት ሰው ሰነፍ ከኾነ (ካልሠራ) ክፉ ድህነት እንደሚመጣበት ተናግሯል /ምሳ.፮፥፱-፲/፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ ‹‹ከእናንተ ሊሠራ የማይወድ አይብላ›› በማለት ሥራ የማይወድ ሰው ምግብ መሻት እንደሌለበት አስረድቷል /፪ኛተሰ.፫፥፲/፡፡

ታዲያ መጽሐፍ ቅዱስ ስንፍናን የሚያወግዝ፣ ሥራን የሚያበረታታ ኾኖ ሳለ ለምንድን ነው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ለነፍሳችሁ በምትበሉት ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፡፡ …›› ሲል ያስተማረው ለሚለው የሰው ልጅ ሠራተኛ ፍጥረት ቢኾንም ዝናም አልጥልለት ሲል፤ የዘራበት መሬት ሳያበቅል ሲቀር፤ የወር ደመወዙ ሲዘገይ፤ እኽል የሚሸምትበት ገንዘብ ሲያጣ፤ ወዘተ. በመሳሰሉት ፈተናዎች ውስጥ በኾነ ጊዜ ምን ልበላ፣ ልጠጣ ነው? ልጆቼ እንዴት ሊኾኑብኝ ነው? ዛሬን እንዴት ላልፍ ነው? በሚሉትና በመሳሰሉት የጭንቀትና የተስፋ መቍረጥ ስሜቶች ሳይያዝ የዕለት ጕርሱን፣ የዓመት ልብሱን ይሰጠው ዘንድ የጠፋውን ዝናም ማምጣት፤ የደረቀውን ዘር ማለምለም፤ ባዶ የኾነውን ቤት መሙላት የሚቻለውን እግዚአብሔርን በእምነት ኾኖ በጸሎት ይጠይቀው ለማለት ነው፡፡

ሲጠቃለል የሰው ልጅ ይርበኛል፣ ይጠማኛል ማለቱን ትቶ በእግዚአብሔር አምሳል መፈጠሩን በማሰብ ዓቅሙ በሚችለው ኹሉ እንዲሠራ፤ የጐደለውን እንዲሞላለት ደግሞ ጸሎቱን ወደ ፈጣሪው እንዲያቀርብ ሲያስረዳ ጌታችን ‹‹ለነፍሳችሁ በምትበሉት፣ ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፡፡ …›› ብሏል፡፡ ስላለፈው ትምህርት ይህንን ያህል ከገለጽን ወደ ዛሬው ዝግጅታችን እናልፋለን፤

በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ከነሐሴ ፳፰ እስከ መስከረም ፩ ቀን (ከአብርሃም እስከ ዮሐንስ) ድረስ ያለው ክፍለ ክረምት ‹‹ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን መዓልት›› ይባላል፡፡ በዚህ ክፍለ ክረምት ውስጥ ባሉት ቀናት በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን እነዚህን ፍጥረታት የሚመለከቱ የቅዱሳት መጻሕፍት ክፍሎች ይነገራሉ፤ ይተረጐማሉ፤ ይመሠጠራሉ፡፡

‹‹ጎሕ፣ ነግሕና ጽባሕ›› ንጋት፣ ማለዳ፣ ሌሊቱ ወደ ቀን፤ ጨለማው ወደ ብርሃን የሚሸጋገርበት ክፍለ ጊዜ የሚል ትርጕም አላቸው፡፡ ብርሃን ደግሞ የጨለማ ተቃራኒ፣ የፀሐይ ብርሃን የማይታይበት ክፍለ ዕለት ሲኾን ‹‹ዕለት›› ማለትም በአንድ በኩል የፀሐይ ብርሃን የሚታይበት ጊዜን፣ በሌላ በኩል ደግሞ ከእሑድ እስከ ሰኞ ያሉትን፣ እንደዚሁም ከ፩-፴ የሚገኙ ዕለታትንም ያመላክታል /ዘፍ.፩፥፭-፴፩/፡፡ በአጠቃላይ ‹‹ጎሕ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን፣ መዓልት›› ኹሉም የግእዝ ቃላት ሲኾኑ ተመሳሳይ ትርጕምና ጠባይዕ ያላቸው ፍጥረታት ናቸው፡፡

ስለ ንጋትና ብርሃን ለመናገር በመጀመሪያ ስለ ፀሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብት አፈጣጠር ማስታዎስ ያስፈልጋል፡፡ ይኸውም እግዚአብሔር አምላክ በዕለተ ረቡዕ በመጀመሪያው ሰዓተ ሌሊት ‹‹ለይኩን ብርሃን፤ ብርሃን ይኹን›› ባለ ጊዜ ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብት ተፈጥረዋል፡፡ የፀሐይ ተፈጥሮዋ ከእሳትና ከነፋስ ሲኾን ጨረቃንና ከዋክብትን ደግሞ ከነፋስና ከውኀ አርግቶ ፈጥሯቸዋል፡፡ ሲፈጥራቸውም ከኹሉም ፀሐይን፤ ከከዋክብት ደግሞ ጨረቃን አስበልጦ ፈጥሯቸዋል፡፡ የፈጠራቸውም እጠቀምባቸዋለሁ ብሎ ሳይኾን ለሰው ልጅና በዚህ ዓለም ለሚገኙ ፍጥረታት እንዲያበሩ ነው፡፡

እነዚህ የብርሃን ምንጮች ልዩ ልዩ ምሳሌያት አሏቸው፤ ጻድቃን ኹልጊዜ በምግባር በሃይማኖት ምሉዓን በመኾናቸው በፀሐይ፤ ኀጥኣን ደግሞ አንድ ጊዜ ሙሉ፣ ሌላ ጊዜ ጐደሎ እየኾኑ ይኖራሉና በጨረቃ ይመሰላሉ፡፡ አካሔዳው በሰማይና በምድር መካከል መኾኑ ምእመናን ጻድቃን በተፈጥሯቸው ምድራውያን ኾነው ሳሉ ሰማያዊውን መንግሥት የመውረሳቸው ምሳሌ ነው፡፡ ሰሌዳቸው ከነፋስ፣ ከእሳትና ከውኀ መኾኑ የመመህራን መንፈሳዊ ቍጣ ምሳሌ ነው፡፡ አንድም እሳት የመለኮት፤ ውኀ የትስብእት፤ ነፋስ የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌ ነው /ሥነ ፍጥረት አንድምታ ትርጓሜ/፡፡

በሌላ ምሥጢር ስንመለከታቸው ‹‹ጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃን መዓልት›› ወይም ኹሉንም በአጠቃላይ በብርሃን ምንጭነት ወይም በብርሃን ብንሰይማቸው ብርሃን እግዚአብሔር ነው፡፡ እርሱ በጨለማው ዓለም፤ በጨለማው ሕይወታችን፤ በጨለማው ኑሯችን የሕይወትን ወጋገን፣ ንጋት፣ ቀን የሚያወጣ አምላክ ነውና /ዮሐ.፩፥፭-፲/፡፡ ስለዚህ ‹‹እግዚአብሔር ብርሃኔና መድኀኒቴ ነው፤ የሚያስፈራኝ ማነው?›› በማለት በብርሃን በተባለ በእግዚአብሔር መታመን ያስፈልገናል /መዝ.፳፮፥፩/፡፡ ዳግመኛም የእግዚአብሔር ሕግ ብርሃን ይባላል፡፡ ብርሃን ጨለማን እንደሚያስወግድ ኹሉ የእግዚአብሔር ሕግም ከኀጢአት ባርነት፣ ከሲኦል እሳት ያድናልና፡፡ ‹‹ሕግህ ለእግሬ መብራት፤ ለመንገዴም ብርሃን ነው›› እንዳለ ቅዱስ ዳዊት /መዝ.፻፲፰፥፻፭/፡፡

እንደዚሁም ብርሃን ክርስቲያናዊ ምግባርን ያመለክታል፡፡ ብርሃን ለራሱ በርቶ ለሌሎችም እንዲያበራ ክርስቲያናዊ ምግባርም ከራስ ተርፎ ለሰዎች ኹሉ ደምቆ ይታያልና /ዮሐ.፲፪፥፴፮፤ ፩ኛ ዮሐ.፩፥፯/፡፡ እኛም ‹‹ብርሃን ሳለላችሁ በብርሃን ተመላለሱ›› ተብሎ እንደ ተጻፈ የጽድቅ ሥራ የማይገኝበት ጊዜ የጨለማ ዘመን ከመምጣቱ በፊት የጽድቅ ሥራ መሥራት በምንችልበት ጊዜ ኹሉ በመልካም ምግባር ጸንተን እንኑር፡፡

ደግሞም መልካም ግብር ያላቸው ምእመናን ብርሃን ተብለው ይጠራሉ፤ ብርሃን በግልጽ ለሰዉ ኹሉ እንደሚታይና እንደሚያበራ መልካም ምግባር ያላቸው ምእመናንም በጽድቅ ሥራቸው ለብዙዎች አርአያ፣ ምሳሌ ይኾናሉና፡፡ ‹‹እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ፡፡ በተራራ ላይ ያለች ከተማ ልትሠወር አይቻላትም›› እንዳለ ጌታችን በወንጌል /ማቴ.፭፥፲፬/፡፡ እንግዲህ ኹላችንም በጨለማ ከሚመሰለው ኀጢአት ወጥተን ወደ ጽድቅ ሕይወት እንመለስና እኛም በርተን ለሌችም ብርሃን እንኹን፡፡ አምላካችን ከኀጢአት ተለይተን፣ ንስሐ ገብተን እንደ ጻድቃኑ ‹‹የዓለም ብርሃን›› ለመባል የበቃን ያድርገን፡፡

በአጠቃላይ ይህ ወቅት ‹‹ቡሄ ካለፈ የለም ክረምት፤ ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት›› እንደሚባለው ክረምቱ እየቀለለ፤ ዝናሙ እያባራ፤ ማዕበሉ እየቀነሰ፤ ሰማዩ እየጠራ የሚሔድበት የንጋት፣ የወጋገን፣ የብርሃን ጊዜ ነው፡፡ ልክ እንደ ዘመኑ እኛም በልባችን የቋተርነውን የቂም ደመና፤ በአእምሯችን የሣልነውን የክፋት ጨለማ፤ በወገን ላይ ያደረስነውን የዝናምና ማዕበል አድማ በንስሐ ፀሐይ አስወግደን ወደ ብርሃኑ ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ፤ ወደ ብርሃኑ ሕገ እግዚአብሔር፤ ወደ ብርሃኑ ምግባረ ሠናይና ወደ ብርሃኑ ክርስትና እንድንመለስ ልዑል እግዚአብሔር ‹‹በሕይወታችሁ ውስጥ ብርሃን ይኹን›› ይበለን፡፡ እርሱ ‹‹ብርሃን ይኹን›› ካለ የኀጢአት ጨለማ በእኛ ላይ ለመሠልጠን የሚችልበት ዓቅም አያገኝምና፡፡

ከአራተኛው ክፍለ ክረምት (ከጎህ፣ ነግህ፣ ጽባሕ፣ ብርሃንና መዓልት) ቀጥሎ የሚገኘው አምስተኛው ክፍል ደግሞ ከመስከረም ፩-፰ ቀን (ከዮሐንስ እስከ ዘካርያስ) ያለው ጊዜ ሲኾን ይኸውም ‹‹ዮሐንስ›› በመባል ይታወቃል፡፡ ይህ ክፍለ ጊዜ የዓዋጅ ነጋሪው መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ትምህርት፣ ጥምቀት፣ ምስክርነት፣ አገልግሎት፣ ዜና ሕይወት፣ ክብር፣ ቅድስና፣ ገድልና ዕረፍት፣ እንደዚሁም ቅዱስ ዮሐንስ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለማጥመቅ መመረጡ ከአዲሱ ዓመት ጋር እየተጣጣመ በስፋት የሚዳሰስበት የብሥራት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ሳምንት የቅዱስ ዮሐንስን አገልግሎት የሚመለከቱ ትምህርቶች በቤተ ክርስቲያን በስፋት ይቀርባሉ፡፡ የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ በረከት በኹላችን ላይ ይደር፡፡

ይቆየን፡፡

ቅዱስ ሩፋኤል መልአከ ሰላም ወጥዒና

ጳጕሜን ፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ዮሴፍ ይኵኖአምላክ

Kidus Rufael

ጳጕሜን ‹‹ጭማሪ፣ ተውሳክ፣ አምስት ቀን ከሩብ›› የሚል ትርጕም አለው፡፡ ወርኀ ጳጕሜን ኢትዮጵያን ብቸኛዋ የዓለማችን ባለ ፲፫ ወራት አገር እንድትኾን ያስቻለች ልዩ ወር ናት፡፡

ጳጕሜን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የዓለም ፍጻሜ መታሰቢያ ተደርጋ ትታሰባለች፡፡ በዚህ የተነሣ በርካታ የቤተ ክርስቲያኒቱ ተከታዮች ወርኀ ጳጕሜን በጾምና በጸሎት /በሱባዔ/ ያሳልፏታል፡፡ በተለይም እንደ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ በቅዱስ ሩፋኤል ዕለት ሰማያት የሚከፈቱበት /ተርኅዎ ሰማይ/ መኾኑን በማመን ምእመናን ወደ ወንዞች በመሔድ እንዲሁም በጳጕሜን ቀናት በሚዘንበው ዝናብ በመጠመቅ በረከትን ይሻሉ፡፡ ጸሎታቸውንም ከምንጊዜውም በበለጠ ያቀርባሉ፡፡

ወርኀ ጳጕሜን የጌታችን ምጽአት የሚታሰብባት በመኾኗ የሚዘመረው መዝሙር፣ የሚነበቡ ምንባባትና ቅዱስ ወንጌሉ እንዲሁም የሚሰበከው ምስባክ ይህንኑ የሚያሳዩ ናቸው፡፡ በወርኀ ጳጕሜን በሚገኘው ሰንበት የሚዘመረው መዝሙርም የሚከተለው ነው፤

‹‹ከመ እንተ መብረቅ ዘይወፅእ እምጽባሕ ወያስተርኢ እስከ ዐረብ ከማሁ ምጽአቱ ለወልደ እግዚአብሔር ምስለ ኀይለ ሰማያት በንጥረ መባርቅት ምስለ አእላፍ መላእክት ወኲሎሙ ሊቃነ መላእክት አክሊለ አክሊላት ዲበ ርእሶሙ ለካህናት፤›› ትርጕሙም፡- ‹‹መብረቅ ከምሥራቅ ወጥቶ እስከ ምዕራብ እንዲታይ በመባርቅት ፍጥነት ሰማያውያን ኀይላት ከብዙ መላእክትና የመላእክት አለቆች ጋር በካህናት ራስ ላይ ያሉት አክሊሎች መገኛ የኾነው የሾህ አክሊል ደፍቶ የእግዚአብሔር ልጅ እንዲሁ ይመጣል›› ማለት ነው፡፡

በወርኀ ጳጉሜን ከሚታሰቡት እና ከሚከበሩት በዓላት መካከል ጳጕሜን ፪ ቀን የሐዋርያው ቅዱስ ቲቶ በዓለ ዕረፍት፣ ጳጕሜን ፫ ቀን የሊቀ መላእክት የቅዱስ ሩፋኤል በዓለ ሢመት፣ ጳጕሜን ፭ ቀን የነቢዩ አሞጽ በዓለ ዕረፍት ይጠቀሳሉ፡፡

በየዓመቱ ጳጕሜን ፫ ቀን የሊቀ መላእክት የቅዱስ ሩፋኤል ዓመታዊ ክብረ በዓል በመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት፣ በልዩ ልዩ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ይከበራል፡፡ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል ከከበሩት ቅዱሳን መላእክት ሦስተኛው ነው፡፡ ‹‹ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ” እንዲል /ጦቢት ፲፪፥፲፭/፡፡

ያለማቋረጥ ፈጣሪያቸውን ልዑል እግዚአብሔርን ከሚያመሰግኑ ቅዱሳን መላእክት መካከል አንዱ መልአከ ጥዒና ወሰላም /የሰላምና የጤና መልአክ/ የሚባለው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ ‹‹ሩፋኤል›› የሚለው የስሙ ትርጓሜ ደስ የሚያሰኝ፣ ቸር፣ መሐሪ፣ ቅን የዋህ ማለት ነው፡፡

የሰው ልጆች ከተያዙበት የኀጢአት ቁስል ይፈወሱ ዘንድ በአማላጅነቱና በጸሎቱ የማይለይ መልአክ ነው፡፡ ‹‹በበሽታ ኹሉ ላይ በሰው ልጆችም ቍስል ላይ የተሾመው ቅዱስ ሩፋኤል ነው›› በማለት ሄኖክ ከእግዚአብሔር መልአክ ያገኘውን የምስክርነት ቃል ጽፏል /ሄኖክ ፲፥፲፫/፡፡ ቅዱስ ሩፋኤል በሰውነታችን ላይ የሚወጣውን ደዌም ኾነ ቍስል ይፈውስ ዘንድ ከልዑል እግዚአብሔር ሥልጣን ተሰጥቶታል፡፡ ‹‹በሰው ቍስል ላይ የተሾመ ከከበሩ መላእክት አንዱ ቅዱስ ሩፋኤል ነው›› እንዳለ ሄኖክ /ሄኖክ ፮፥፫/፡፡

ለቈሰሉ ፈውስን የሚያሰጣቸው ለማኅፀን ችግር ኹሉ ለሴቶች ረዳታቸው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ ሴት በፀነሰችበት ወቅት ቅዱስ ሩፋኤል አይለያትም ሕፃኑ ዐርባ ቀን ሞልቶት፣ በማኅፀን እያለ ‹‹ተሥዕሎተ መልክዕ›› (በሥላሴ አርአያ መልኩ መሳል) ከጀመረበት ቀን አንሥቶ እስከሚወለድበት ቀን ድረስ ቅዱስ ሩፋኤል አይለየውም፡፡ በወሊዳቸው ቀን ሴቶች ከሚደርስባቸው ጭንቀትና ሕመም ስሙን ጠርተው ይማጸኑታል፡፡ ፈታሔ ማኅፀን ነውና ቅዱስ ሩፋኤልም ጭንቀታቸውን ያቀላል፡፡

አስማንድዮስ የተባለ ጋኔን በወለተ ራጉኤል ላይ አድሮ ባሎቿን እየገደለ ቢያሰቃያት ቅዱስ ሩፋኤል ጋኔኑን አስጨንቆ አስወጥቶላታል /ጦቢት ፫፥፰-፲፯/፡፡ ቅዱስ ሩፋኤል ‹‹ዳግመኛም እግዚአብሔር ሩፋኤልን፣ አዛዝኤልን እጁን እግሩን አስረህ በጨለማ ውስጥ ጣለው አለው›› ተብሎ እንደ ተጻፈ /ሄኖክ ፫፥፭-፯/ ለቃየን ልጆች ሰይፍና ሾተል መሥራትን፣ የምንዝር ጌጥ ማጌጥን፣ መቀንደብን ያስተማረ አዛዝኤል የተባለውን ጋኔን በእሳት ሰይፍ እየቀጣ በረቂቅ አስሮ ወደ ጥልቁ የጣለው ይኸው መልአክ ቅዱስ ሩፋኤል ነው /ሄኖክ ፪፥፲፰/፡፡

የጦቢትን ልጁ ጦቢያን በሰው አምሳል ተገልጦ ከተራዳው በኋላ ወደ ሰማይ በሚያርግበት ጊዜ ራሱን ሲገልጥ ‹‹የቅዱሳንን ጸሎት ከሚያሳርጉ ወደ ከበረ ወደ ገነነ ወደ እግዚአብሔር ጌትነትም ከሚያገቡ ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ አላቸው›› /ጦቢት ፲፪፥፲፭/፡፡

የቅዱስ ሩፋኤል በዓሉ የሚከበርባቸው ምክንያቶችም ሁለት ናቸው፡፡ እነርሱም አንደኛው በዓለ ሢመቱን ምክንያት በማድረግ ሲኾን ሁለተኛው ደግሞ ቅዳሴ ቤቱ ነው፡፡ በቅዱስ ሩፋኤል ተራዳዒነት ከተደረጉ ተአምራት መካከል በእስክንድርያ አቅራቢያ በምትገኝ ደሴት በታነጸች ቤተ ክርስቲያኑ ያረገው ተአምር አንደኛው ነው፡፡

በመጽሐፈ ስንክሳር እንደ ተጻፈው ብዙ ምእመናን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እያሉ ቤተ ክርስቲያኒቱ ፈጽማ ተናወጸች፤ ያቺ ደሴት በታላቅ አንበሪ ጀርባ ላይ የቆመች ናትና፡፡ የሰዎች ብዛትም በከበደው ጊዜ ዓሣ አንበሪው ቤተ ክርስቲያኒቱን ያፈርሳት ዘንድ ሰይጣን አነሣሣው፡፡ ወደ ክብር ባለቤት እግዚአብሔርም በከበረ መልአክ ሩፋኤል ስም ጮኹ፡፡ ያን ጊዜ ቅዱስ ሩፋኤል ያንን አንበሪ በጦሩ ወግቶ ‹‹እግዚአብሔር አዝዞሃልና ከቦታህ ሳትናወጽ ጸጥ ብለህ ቁም!›› ባለው ጊዜ አንበሪው ጸጥ ብሎ ቆመ፤ በውስጧም ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ፤ ለሕሙማንም ፈውስ ኾነ፡፡ የቅዱስ ሩፋኤል ተራዳዒነት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

 

ተዝካረ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ጻድቅ

ነሐሴ ፳፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዝግጅት ክፍሉ

Tkle

አቡነ ተክለ ሃይማኖት

በዛሬው ዝግጅታችን ነሐሴ ፳፬ ቀን የሚከበረውን በዓለ ዕረፍታቸውን ምክንያት በማድረግ ከቅዱሳን ጻድቃን መካከል አንዱ የኾኑትን፣ ‹‹ሐዲስ ሐዋርያ›› እየተባሉ የሚጠሩትን የቅዱስ ተክለ ሃይማኖትን ዜና ሕይወት በአጭሩ ይዘን ቀርበናል፤

አቡነ ተክለ ሃይማኖት በእግዚአብሔር መልካም ፈቃድ፣ በሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ብሥራት፤ ከአባታቸው ከካህኑ ጸጋ ዘአብና ከእናታቸው ከቅድስት እግዚእ ኀረያ ታኅሣሥ ፳፬ ቀን ፲፪፲፪ ዓ.ም. በቡልጋ አውራጃ በደብረ ጽላልሽ ኢቲሳ ተወለዱ፡፡ በተወለዱ በሦስተኛውም ቀን እሑድ ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት ከእናታቸው ዕቅፍ ወርደው ‹‹አሐዱ አብ ቅዱስ፤ አሐዱ ወልድ ቅዱስ፤ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ፡- አንዱ አብ ቅዱስ ነው፤ አንዱ ወልድ ቅዱስ ነው፤ አንዱ መንፈስ ቅዱስ ቅዱስ ነው›› በማለት ሥላሴን አመስግነዋል፡፡ ወላጆቻቸውም ስማቸውን ‹‹ፍሥሐ ጽዮን›› ብለዋቸዋል፡፡ በተወለዱ በ፲፭ ዓመታቸው ዲቊናን፤ በ፳፪ ዓመታቸው ቅስናን ከግብፃዊው ጳጳስ ከአባ ጌርሎስ /ቄርሎስ/ ተቀብለዋል፡፡

አንድ ቀን ወደ ጫካ ለአደን በሔዱበት ዕለት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱ ክርስቶስ ተገልጦላቸው ጸጋ መንፈስ ቅዱን ካሰደረባቸው፤ እንደዚሁም ‹ሐዲስ ሐዋርያ› ብሎ ወንጌል ወዳተዳረሰበት ቦታ እንደሚልካቸው ከነገራቸው፤ ቅዱስ ሚካኤልም ከአውሬ አዳኝነት ሰውን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመመለስ እንደ ተመረጡና አጋንንትን የማውጣት፣ ተአምራትን የማድረግ ሥልጣን እንደ ተሰጣቸው፤ ስማቸውም ‹ተክለ ሃይማኖት› እንደሚባልና ትርጓሜውም ተክለ አብ፣ ተክለ ወልድ፣ ተክለ መንፈስ ቅዱስ ማለት ነው›› እንደ ኾነ ካስረዳቸው በኋላ ወደ ቤታቸው ተመልሰው ያላቸውን ንብረት ኹሉ ለቤተ ክርስቲያንና ለነዳያን ሰጥተው ‹‹አቤቱ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! የመንግሥተ ሰማያትን በር ትከፍትልኝ ዘንድ እነሆ ቤቴን እንደ ተከፈተ ተውኩልህ›› በማለት ቤታቸውን ትተው ወንጌልን ለማስተማር ፈጥነው ወጡ፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምረው በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ ወንጌልን በመስበክና ተአምራትን በማድረግ ብዙ አሕዛብን ከአምልኮተ ጣዖት ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር፤ ከገቢረ ኀጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ መልሰዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንንም አንጸዋል፡፡

ከዚህ በኋላ በደብረ ሊባኖስ (ገዳመ አስቦ) ዋሻ በመግባትም ሁለቱን በፊት፣ ሁለቱን በኋላ ሁለቱን በቀኝ፣ ሁለቱን በግራ ስምንት ጦሮችን ተክለው እጆቻቸውን በትእምርተ መስቀል በመዘርጋት የክርስቶስን ሕማም፣ ሞትና ነገረ መስቀል በማሰብ በተመስጦ ሌሊትና ቀን ያለማቋረጥ በጾም፣ በጸሎት ተወስነው ሲጋደሉ፤ ከቊመት ብዛት የተነሣ በ፺፪ኛ ዓመታቸው ጥር ፬ ቀን ፲፪፹፱ ዓ.ም አንዲቱ የእግራቸው አገዳ ተሰብራለች፡፡ ደቀ መዛሙርቱም የመንፈሳዊ አባታቸውን ስባረ ዐፅም አክብረው በሥርዓት አኑረዋታል፡፡ እግራቸው እስኪሰበር የቆዩባቸው ዓመታትም ፳፪ ናቸው፡፡ ለሰባት ዓመታት በአንድ እግራቸው ቆመው ያለ ምግብና ያለ ውኃ በትኅርምት ሌሊትና ቀን እንደ ምሰሶ ጸንተው በትጋት ለሰው ዘር ኹሉ ድኅነትን ሲለምኑ ኖረዋል፡፡

ከሰባቱ ዓመታት ውስጥ ጥቂት ውኃ የቀመሱት በአራተኛው ዓመት ብቻ እንደ ነበረ መጽሐፈ ገድላቸው ይናገራል፡፡ ጻድቁ አባታችን ምድራዊ ሕይወታቸውን በተጋድሎና በሐዋርያዊ አገልግሎት ከፈጸሙ በኋላ ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ የሚያልፉበት ቀን በተቃረበ ጊዜ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም፣ ከቅዱሳን መላእክት፣ ከቅዱሳን ነቢያትና ከቅዱሳን ሐዋርያት ጋር ወደእርሳቸው በመምጣት የሚያርፉበት ዕለት መድረሱን ነግሯቸው የተጋድሏቸውን ጽናት አድንቆ በስማቸው መታሰቢያ ለሚያደርጉ፣ ለነዳያን ለሚመጸዉቱ ቤተ ክርስቲያን ለሚያሠሩ የምሕረት ቃል ኪዳን ሰጥቷቸው በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ ስለ ተጋድሏቸው ጽናትም ‹‹በሰው እጅ የማይለካውን ይህንን የመንግሥት አዳራሽ ውሰድ›› በማለት የመለኮትን ነገር የሚናገር የእሳት አንደበት ያለው የጸጋ ልብስ አልብሷቸዋል፤ በመስቀል ምልክት ያጌጡ ሰባት የሕይወት አክሊላትንም አቀዳጅቷቸዋል፡፡

አቡነ ተክለ ሃይማኖትም የዕረፍታቸው ጊዜ መቃረቡን ባወቁ ጊዜ የመንፈስ ልጆቻቸውን ጠርተው ጌታችን የነገራቸውን ሁሉ አስረድተው አባታዊ ምክርና ተግሣፅ ከሰጧቸው በኋላ ነሐሴ ፳፬ ቀን ከዚህ ዓለም ድካም ዐረፉ፡፡ የመንፈስ ልጆቻቸውም ለአንድ ቅዱስ አባትና ካህን በሚገባ ሥርዓት በማኅሌት፣ በዝማሬና በምስጋና ቀበሯቸው፡፡ ጌታችንም ከእመቤታችንና ከቅዱሳን መላእክት ጋር ተገልጾ ታያቸው፤ ነፍሳቸውንም ‹‹የጠራሽ፣ ንጽሕት ነፍስ ሆይ ወደእኔ ነዪ›› ብሎ በክብር ተቀብሏታል፡፡ በመጽሐፈ ገድላቸው እንደተጠቀሰው ቅዱስ አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት በዚህ ዓለም የኖሩበት ዕድሜ ዘጠና ዘጠኝ ዓመት ከዐሥር ወር ከዐሥር ቀን ነው፡፡ ገድላቸው ዕድሜያቸውን በመከፋፈል፡- በእናት አባታቸው ቤት ፳፪ ዓመት፤ በከተታ ፫ ዓመት፤ በይፋት ፱ ወር፤ በዳሞት ፲፪ ዓመት፤ በአማራ ፲ ዓመት፤ በሐይቅ ፲ ዓመት፤ በደብረ ዳሞ ፲፪ ዓመት፤ በትግራይ ገዳማት በመዘዋወርና ወደ ኢየሩሳሌም በመመላለስ ፩ ዓመት፤ ዳዳ በሚባል አገር ፩ ወር፤ በደብረ አስቦ ገዳም ፳፱ ዓመት ከ፲ ቀን መቆየታቸውን ይናገራል /ገ.ተ.ሃ.፶፱፥፲፬-፲፭/፡፡

በአጠቃላይ አባታችን ተክለ ሃይማኖት ሕይወታቸዉን ሙሉ ለእግዚአብሔር በመስጠት፣ እንደ በሬ ተጠምደው፣ እንደገበሬ ታጥቀው ይህንን ዓለም ንቀው በጾም በጸሎት ተወስነው በብሕትውና ከመኖራቸው በተጨማሪ እንደቅዱሳን ሐዋርያት ወንጌልን በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ የሰበኩ፣ በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ድውያነ ሥጋን በተአምራት፣ ድውያነ ነፍስን በትምህርት የፈወሱ ሐዋርያ ናቸው፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያችንም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ ‹‹እናንተን የሚቀበል እኔን ይቀበላል፤ እኔንም የሚቀበል የላከኝን ይቀበላል፡፡ ነቢይን በነቢይ ስም የሚቀበል የነቢይን ዋጋ ያገኛል፡፡ ጻድቅንም በጻድቅ ስም የሚቀበል የጻድቁን ዋጋ ያገኛል፡፡ ማንም ከእነዚህ ከተናናሾቹ ለአንዱ ቀዝቃዛ ጽዋ ብቻ በደቀ መዝሙር ስም የሚያጠጣ እውነት እላችኋለሁ፤ ዋጋው አይጠፋበትም›› /ማቴ.፲፥፵-፵፪/ በማለት የተናገረውን መለኮታዊ ቃል ኪዳን መሠረት አድርጋ መጋቢት ፳፬ ቀን ፅንሰታቸውን፤ ታኅሣሥ ፳፬ ቀን ልደታቸውን፤ ጥር ፳፬ ቀን ስባረ ዐፅማቸውን፤ ግንቦት ፲፪ ቀን ፍልሰተ ዐፅማቸውን ነሐሴ ፳፬ ቀን ዕረፍታቸውን በትላቅ ደስታ ታከብራለች፡፡

ቅዱሳን ጻድቃን በመንፈሳዊ አርአያነታቸው፣ በጸሎታቸውና በትምህርታቸው ከከበቡን የነፍስ ጠላቶች፤ ከርኲሳን መናፍስትና ከጨለማው ልጆች፣ ከክፉ ሰዎች ሽንገላና ተንኰል ለመሰወርና ለመጠበቅ ከእግዚአብሔር የተቀበሉት ሥልጣን ምን ጊዜም ይሠራል፡፡ በጻድቃን መኖር ሀገር ከጥፋት ትድናለች፡፡ የጻድቃንን ስም ጠርቶ እግዚአብሔርን በመለመን በረከትና ረድኤት ይገኛል፡፡ ስለ ጻድቃን ብሎ እግዚአብሔርም ምሕረቱን ያድላል፡፡ ጻድቃንን ማሰብ ሥራቸውን መዘከር ክርስቲያናዊ ሕይወታችንን ያጐለምሳል፡፡ በነፍስ በሥጋ ይታደገናል፤ ይረባናል፤ ይጠቅመናል፡፡ ስለዚህም ነው ቤተ ክርስቲያናችን ጻድቃንን እንድናስባቸው፣ በስማቸውም ለድሆችና ለጦም አዳሮች እንድንመጸውት መታሰቢያቸውን እንድናደርግ የምትመክረን፤ የምታስተምረን /ማቴ.፲፥፵፩-፵፪/፡፡ ጻድቃንን በሕይወተ ሥጋ ሳሉም ቢኾን፤ ከሞቱም በኋላ በዐጸደ ነፍስ በጸሎታቸው ለሚታመኑ፣ በቃል ኪዳናቸው ለሚማጸኑ፣ የድኅነተ ሥጋ፣ የድኅነት ነፍስ ምክንያቶች ናቸው፡፡

የአቡነ ተክለ ሃይማኖትና የኹሉም ጻድቃን ጸሎትና በረከት ረድኤትና ምልጃ በመላው ሕዝበ ክርስቲያን ላይ ጸንቶ ይኑር፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡-

መለከት መጽሔት ፲፰ኛ ዓመት፣ ቍጥር ፱፡፡

መጽሐፈ ስንክሳር፣ ነሐሴ ፳፬ ቀን፡፡

ገድለ ተክለ ሃይማኖት፡፡

ክብረ ድንግል ማርያም

ነሐሴ ፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ታደለ ፈንታው

mariam[1]

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከተወደደ ልጇ ጋር

እግዚአብሔር ዘላለማዊ ኃይሉንና አምላክነቱን ለዓለም ከገለጸበት ታላቅ ሥራ መካከል በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም የገለጸው ድንቅ ሥራው በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ቀዳሚውን ሥፍራ ይይዛል፡፡ ይህንን ኹኔታ ድንግል ማርያም ‹‹ብርቱ የኾነ እርሱ ታላቅ ሥራን በእኔ አድርጓል፤ ስለዚህም ፍጥረት ኹሉ ያመሰግኑኛል›› /ሉቃ.፩፥፵፱/ በማለት ገለጸችው፡፡

ቅድስት ኤልሳቤጥም ‹‹የጌታዬ እናት›› አለቻት /ሉቃ.፩፥፵፫/፡፡ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ‹‹ከሴቶች መካከል ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ›› አላት /ሉቃ.፩፥፳፰/፡፡ ቅዱስ ዳዊት ደግሞ ‹‹ልጄ›› ይላታል /መዝ.፵፬፥፱/፡፡ ሰሎሞንም ‹‹እኅቴ›› ይላታል /መኃ.፭፥፩/፡፡ ለወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስም እናት ኾና ተሰጥታዋለች /ዮሐ.፲፱፥፳፮/፡፡ ይህን ድንቅ ምሥጢር ውስንና ደካማ የኾነ አእምሮ ሊገነዘበው ከሚችለው በላይ ነው፡፡

ቅዱስ አግናጥዮስ ዘአንጾኪያ ለኤፌሶን ክርስቲያኖች በጻፈው መልእክቱ እንደገለጸው ‹‹የቅድስት ማርያም ዘለዓለማዊ ድንግልና፤ አማኑኤልን መውለዷና የማይሞተው ጌታ መሞቱ›› እነዚህ ሦስቱ ከዚህ ዓለም ጥበበኞችና ገዢዎች የተሰወሩ ምሥጢራት ናቸው፡፡ ቅዱስ አግናጥዮስ ‹‹እነዚህ ድንቅ ምሥጢራት በራሳቸው ከንግግርና ከቋንቋዎች ኹሉ በላይ ኾነው የሚነገሩ በእግዚአብሔር የዝምታ መጐናጸፊያ የተጠቀለሉ ድብቅና ጣፋጭ ምሥጢሮች ናቸው›› ይላል፡፡

የእመቤታችን ምስጋናዋ የበዛለት ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊም ‹‹አቤቱ መሰንቆ ልቡናዬን አነቃቃ፤ የልቤንም እንዚራ፡፡ ድምፁን ከፍ አድርጎ የዳዊት ልጅ የኾነችውን፣ የጌታውን እናት ድንግል ማርያምን ያመሰግናት ዘንድ፤ ለዓለም ሕይወት የሚሰጠውን የወለደች እናቱ የኾነች እርሷን ከፍ ከፍ ያደርጋት ዘንድ›› ብሏል፡፡ በሌላም አንቀጽ ደግሞ ‹‹ከሕሊናት ኹሉ በላይ ለኾነ ለዚህ ነገር አንክሮ ይገባል፡፡ ምድራዊት ሴት ፈጣሪዋን ወለደችው፤ እርሱም እናቱን ፈጠረ›› አለ፡፡ ስለእነዚህ ነገሮች ኹሉ ምን ማለትን እንችላለን? እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ስለ ድንግል ማርያም ያልተናገረበት ጊዜ፤ ያላናገረው ቅዱስ እንደሌለ እንመለከታለን፡፡

‹‹በእግዚአብሔር፣ በመላእክትና በሰው ፊት የከበረ ሰው መታሰቢያው ለዘለዓለም ነው፡፡ በቤቱ በቅጥሩ የማይጠፋ የዘለዓለም ስምን ይቀበላልና›› /ኢሳ.፶፭፥፫/፡፡ ይህንን ታላቅ በረከት እንደሚሰጣቸው የተናገረው የማይዋሸው ቅዱስ እግዚአብሔር ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ወልድ እናት ከድንግል ማርያም የበለጠ በሰውና በእግዚአብሔር ዘንድ የከበረ ማንን ልንጠራ እንችላለን? እንደ እርሷስ ሊታሰብ፣ ሊከበርም የሚችል በቅድስና ሕይወት ያለፈ ማን ይኖራል?

ቅዱስ እግዚአብሔር ፍጥረቱንና ዓለሙን ለማዳን የወሰነው ጊዜ በደረሰ ጊዜ ከድንግል ማርያም በድንግልና ተወለደ፡፡ አስቀድሞ በመልአኩ አፍ እንዳናገረ ክብሩ በእርሷ ላይ ታየ /ኢሳ.፷፥፪/፡፡ ማኅፀኗን ከተማ አድርጎ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በእርስዋ አደረ፡፡ መንፈስ ቅዱስ በእመቤታችን ላይ የማደሩ ምሥጢር ያነጻቸው፤ ይቀድሳቸው፤ በሥጋም በነፍስም መርቶ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ያገባቸው ዘንድ በነቢያት፣ በሐዋርያት ላይ እንዳደረው ዓይነት አይደለም፡፡ ከሦስቱ አካል አንዱ አካል እግዚአብሔር ወልድ (ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ) ከሥጋዋ ሥጋን፣ ከነፍስዋ ነፍስን ነስቶ ፍጹም ሰው፣ ፍጹም አምላክ ኾነ እንጂ፡፡ ቅዱስ ሉቃስ ይህን ዘለዓለማዊ እውነት ‹‹መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፤ የልዑል ኃይልም ይጸልልሻል፡፡ ስለዚህ ከአንቺ የሚወለደው ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል›› በማለት ገልጾታል /ሉቃ.፩፥፵፭/፡፡

ኢትዮጵያዊው ሊቅ ደራሲና ገጣሚ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም ‹‹የእስራኤል ንጉሥ በእስራኤል ልጅ አደረ፤ የዳዊት አምላክ ከዳዊት ልጅ ሥጋን ለበሰ፡፡ የዕብራውያን ጌታ በዕብራውያን ልጅ ማኅፀን ተወሰነ፡፡ ለአብርሃም የዕብራይስጥ ልሳን ያስተማረው ከቀድሞም ያልሰማውን ልሳን እንዲናገር አፉን ጆሮውን የከፈተለት ከዕብራዊት ድንግል ተወለደ፤ በድንግልና ወተት ጥቂት ጥቂት እያለ አደገ፡፡ የሕፃናትን ሥርዓት እንዳያጎድል አፉን የሚፈታባት ዘመን እስኪፈጸም ጥቂት ጥቂት እያለ በዕብራይስጥ ልሳን ሲናገር ኖረ፡፡ ለሙሴ በዕብራይስጥ ልሳን በጣቶቹ የተጻፉትን ዐሠርቱ ቃላትን የሰጠ የዕብራይስጥ ፊደል ለመማር ከመምህር እግር በታች ተቀመጠ፡፡ የባቢሎን አውራጃ በምትኾን ሰናዖርም የፍጥረትን ሁሉ ቋንቋ የበተነ እርሱ የአሕዛብን ቋንቋ እንደማያውቅ ኹሉ እናቱ አፍ በፈታችበት ልሳን በዕብራይስጥ ልሳን ሲናገር ኖረ፡፡ ጆሮ ይህንን ነገር ከመስማት የተነሣ የሚለመልምበት ይህ ነገር ዕፁብ ድንቅ ነው፡፡ ለዚህ አንክሮ ይገባል›› አለ፡፡ ይህ በሰው ጥበብ በብራናና በቀለም የተጻፈ እውነት ሳይኾን ለድኅነት በተጠሩ ሰዎች ሁሉ ልቡና በአምላክ ጥበብ የተጻፈ እውነት ነው፡፡

የእናታችን የቅድስት ድንግል ማርያም በረከት ይደርብን፤ የልጇ የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክረስቶስ ጸጋ ይብዛልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በዓለ ፍልሰታና ሻደይ

ነሐሴ ፲፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በሰቆጣ ማእከል

ሻደይ

ልጃገረዶች የሻደይን በዓል ሲጫወቱ

በአገራችን ኢትዮጵያ በተለይ በሰሜኑ ክፍል ሕዝበ ክርስቲያኑ ለረጅም ዘመናት ሥርዓተ አምልኮ ሲፈጸሙባቸው የነበሩና አሁንም እየተፈጸመባቸው የሚገኙ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ መንፈሳውያን ቅርሶች በርካቶች ናቸው። ከእነዚህ ቅርሶች መካከልም መንፈሳውያን በዓላት የሚከበሩበት ሥርዓት አንደኛው ነው፡፡ ከእነዚህ መንፈሳውያን በዓላት ውስጥ በዋግ ኽምራ ሀገረ ስብከት ምእመናን ዘንድ የሚከበረው የሻደይ ምስጋና (ጨዋታ) ልጃገረዶች በአማረ ልብስ ደምቀው ‹‹አሸንድዬ›› በሚባል የቄጠማ ጉንጉን ወገባቸውን አሥረው እየተጫወቱ የሚያከብሩት በዓል ነው።

ከነሐሴ ፲፮ እስከ ነሐሴ ፳፩ ቀን ድረስ የሚከበረው ይህ በዓል በዋግ ኽምራ ‹‹ሻደይ››፣ በላስታ ‹‹አሸንድዬ››፣ በትግራይ ‹‹አሸንዳ››፣ በቆቦ አካባቢ ‹‹ሶለል››፣ በአክሱም አካባቢ ደግሞ ‹‹ዓይነ ዋሪ›› እየተባለ ይጠራል።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት የሻደይ በዓል መጽሐፍ ቅዱሳዊ መነሻ አለው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንትና እንደሚናገሩት የአዳም ከገነት መባረር፣ የኖኅ ዘመን የጥፋት ውኃ፣ የዘመን መለወጫ፣ የመጥመቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ አንገት መቈረጥ፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ (ፍልሰታ) እና የመሥፍኑ ዮፍታሔ ልጅ ታሪክ ከሻደይ በዓል ተያያዥነት ያላቸው ሲኾን በተለይ የእመቤታችን ትንሣኤ (በዓለ ፍልሰታ) ከሻደይ በዓል ጋር የጎላ ግንኙት እንዳለው የቤተ ክርስቲያን መምህራንና የአገር ሽማግሌዎች ይናገራሉ፡፡ እያንዳንዱ ታሪክ ከሻደይ በዓል ጋር ያለውን ግንኙነት በአጭሩ እንመልከት፤

የአዳም ከገነት መባረር

አባታችን አዳም ሕገ እግዚአብሔርን በመተላለፉ ጸጋ እግዚአብሔር ርቆት እርቃኑን በኾነ ጊዜ አካሉን ለመሸፈን የበለስ ቅጠል ማገልደሙን ለማስታዎስና አዳምና ሔዋን ክብራቸውን ተገፈው ከገነት የተባረሩባትን ዕለት ለማሰብ በወቅቱ ያገለደሙትን ቅጠል በምልክትነት በመውሰድ ልጃገረዶች የሻደይ ቅጠልን በገመድ ላይ ጎንጉነው በወገባቸው አገልድመው ያሥራሉ፡፡ አዳምና ሔዋን ከገነት ከመውጣታቸው በፊት ግብረ ሥጋ ግንኙነት ያልጀመሩ ደናግላን ስለነበሩ ያንን በመከተልና በምሳሌነት በመውሰድ ያላገቡ የአገው ልጃገረዶች ተሰባስበው የሻደይ ጨዋታን መጫወት ወይም ማክበር እንደጀመሩ ይነገራል።

የሻደይ በዓልና የጥፋት ውኃ

በኖኅ ዘመን ከተላከው የጥፋት ውኃ በኋላ ውኃው መጕደሉንና አለመጕደሉን እንድታጣራ ኖኅ ርግብን በላካት ጊዜ በምድር ሰላም መኾኑን የለመለመ የወይራ ቅጠል ይዛ በመምጣት ለኖኅ የምሥራች ነግራዋለች። ከዚሁ ጋር በተገናኘ በዓሉን ያንን ለምለም ቅጠል ወገባቸው ላይ በማሰር ከጨለማ ወደ ብርሃን ተሸጋገርን ሲሉ ማክበር እንደጀመሩ አበው ከታሪኩ ጋር አያይዘው ያስቀምጡታል።

የሻደይ በዓልና የመሥፍኑ ዮፍታሔ ልጅ ታሪክ

ዮፍታሔ ወደ ጦርነት በሔደ ጊዜ በድል ከተመለሰ ወደ ቤቱ ሲመለስ መጀመሪያ የሚቀበለውን ሰው እንደሚሠዋ ስእለት ተስሎ ነበር፡፡ ድል አድርጎ ሲመለስም ያለ ወትሮዋ ልጁ እየዘፈነች ልትቀበለው ወጣች፤ በዚህም በጣም አዘነ። ልጁም ለአምላኩ የገባውን ስእለት እንዳያስቀር ብላ ሁለት ወር ስለ ድንግልናዋ አልቅሳ ስእለቱን እንዲፈጽም ጠይቃው ከሁለት ወር በኋላ ልጁን ሠውቷታል፡፡ አባቷ የገባውን ቃል ኪዳን እንዳያጥፍ በማበረታታት በመሥዋዕትነት የቀረበችውን የዮፍታሔን ልጅ በማሰብ በየዓመቱ እየተሰባሰቡ ሙሾ ያወጣሉ፡፡

የልጃገረዶች የቡድን አመሠራረት

በሻደይ በዓል የልጃገረዶች የቡድን አመሠራረት ደብርን (አጥቢያን) መሠረት ያደረገ ነው፡፡ የሻደይ ጨዋታ በዓል በሚያከብሩበት ጊዜ ልጃገረዶች የተለያዩ ባሕላዊ አልባሳትን ለብሰው ከበሮ እና ለምስጋና የሚያስፈልጉ ነገሮችን በማሟላት ተጠራርተው በመጀመሪያ ወደ አጥቢያቸው በመሔድ የቤተ ክርስቲያኑን በር አልፈው ዘልቀው ጣዕመ ዝማሬ እያሰሙ ሦስት ጊዜ ይዞሩና ደጃፉን ተሳልመው በቅጥር ግቢው አመቺ ቦታ ፈልገው ምስጋናቸውን ይጀምራሉ፡፡

ከበሯቸውን እየመቱ፣ የታቦቱን ስም እየጠሩ በሚያምር ድምፃቸው፣ ሽብሻቦ፣ ውዝዋዜ፣ ጥልቅ መልእክትን በያዙ ግጥሞች፣ ለዚህ ያደረሳቸውን አምላክና ታቦት ያወድሳሉ፣ ያሞግሳሉ፣ ያከብራሉ፣ ያመሰግናሉ፡፡ ምስጋናው ለዚህ ዓመት ያደረሳቸውን አምላክ ቀጣዩ ዓመትም እንደዚሁ የሰላም፣ የጤና የተድላ እንዲኾን የሚማጸኑበት፣ ተስፋቸውን የሚገልጹበትና ስእለት የሚሳሉበት በመኾኑ ምስጋናቸውን ሞቅ፣ ደመቅ አድርገው በአንድነት፣ በፍቅር፣ በደስታ፣ በመተሳሰብና በሰላም ይጫወታሉ፡፡ ‹‹ለእግዚአብሔርና ለደብራችን ታቦት ያልኾነ›› እያሉ ጉልበታቸውን፣ ችሎታውንና ልምዳቸውን ሳይቈጥቡ በምስጋናው ይሳተፋሉ።

ከቤተ ክርስቲያን መልስ በአካባቢው ወዳሉት ታላላቅ አባቶች ዘንድ ሔደው በመዘመር ቡራኬ ይቀበላሉ። ከዚያም ተመልሰው ወደ ተራራማ ሥፍራ በመውጣት ክብ ሠርተው ይዘምራሉ፡፡ የዝማሬዎቻቸው ግጥሞችና ዜማዎችም መንፈሳዊ ይዘት ያላቸውና ከግለሰባዊ ስሜት ወይም ከግለሰብ ውዳሴ የራቁ ናቸው፡፡ አጥቢያቸውን እንደማያስደፍሩና እንደሚጠብቁ በምስጋናቸው ይገልጻሉ፡፡ የወከሉትን ደብር ታቦት ስም እየጠሩ ለአባት እናት፣ ለቤተሰብ ጤና፣ ጸጋ፣ ሀብት፣ ሰላም በአጠቃላይ መልካሙን ኹሉ እንዲያደርግላቸው እግዚአብሔርን ይማጸናሉ፡፡

የምስጋናቸው ዜማና ግጥም ተመሳሳይ ቢኾንም የወከሉትን ደብር ስም ብቻ በማቀያየር በተመሳሳይ ዜማ ማወደስ እና መማጸን በኹሉም የሻደይ ተጨዋች ቡድኖች ይስተዋላል፡፡ ልጃገረዶቹ በዚህ የምስጋና ጊዜ የሚሰበስቧቸውን ስጦታዎችም ለቤተ ክርስቲያን ያበረክታሉ።

የሻደይ በዓልና ፍልሰታ

የሻደይ በዓል አጀማመርን በተመለክተ ከላይ ከተቀመጡት ታሪኮች በተጨማሪ በአካባቢው ሕዝብና በቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ዘንድ ተደጋግሞ የሚነሣው ታሪክ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ በዓል ነው፡፡ እግዚአብሔር ለአዳምና ሔዋን ከአምስት ሺሕ አምስት መቶ ዓመት በኋላ ወደዚህ ዓለም አንድያ ልጁን ልኮ ከኀጢአት እሥራት ነጻ እንደሚያወጣቸው በገባላው ቃል ኪዳን መሠረት አምላክ የተወለደባት እና ትንቢቱ የተፈጸመባት፣ ከገነት የተባረረው የሰው ልጅ ወደ ገነት እንዲመለስ ምክንያት የኾነችው፣ የሰው ልጆች መመኪያ የተባለች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከዚህ ዓለም ድካም ካረፈች በኋላ ሞትን ድል አድርጋ ከመቃብር ተነሥታ ወደ ሰማይ ዐርጋለች፡፡

በፍልሰታ ወቅት በዓሉ መከበሩም ለሻደይ ተጨዋቾች ተምሳሌትና የድንግልናቸው አርአያ የሚያደርጓት ድንግል ማርያም አካላዊ ሥጋዋ ከጌቴሰማኒ ወደ ገነት መፍለሱን፤ እንደዚሁም በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር ከነበረበት መነሣቱን ምክንያት በማድረግ እንደኾነ የሚገልጹት የዋግ ኽምራ ሀገረ ስብከት ስብከተ ወንጌል መምሪያ ሓላፊ መጋቤ ምሥጢር ገብረ ሕይወት ኪዳነ ማርያም ‹‹የሻደይ በዓል በልጃገረዶች ዘንድ ተወዳጅ የኾነው በሔዋን ምክንያት የተዘጋው ገነት በእመቤታችን አማካኝነት በመከፈቱ ነው። እመቤታችን መመኪያቸው ስለ ኾነች ልጃገረዶች በዓሉን በደስታ ያከብሩታል፤ ድንግልናቸውንም አደራ የሚሉት ለእርሷ ነው›› ሲሉ ይናገራሉ።

እመቤታችን በነሐሴ ፲፮ ቀን በቅዱሳን መላእክት ሽብሸባ፣ ዕልልታና ዝማሬ ታጅባ ከምድር ወደ ሰማይ ስታርግ ሐዋርያት በታላቅ ደስታ ይመለከቱ፣ ይደነቁም ነበር፡፡

ደናግልም ከቅዱሳን መላእክት ከተመለከቱት ሥርዓት በመነሣት ነጫጭ ልብሶችን ለብሰው፣ አምረውና አጊጠው፣ ረጃጅምና ለምለም ቅጠል በወገባቸው አሥረው  እንደ መላእክቱ አክናፍ ወገባቸውን ከግራ ወደ ቀኝ እያመላለሱ፣ እያዘዋወሩና እያሸበሸቡ፣ በአንደበታቸው እየዘመሩና በእጆቻቸው እያጨበጨቡ በአንድነት ተሰባሰባስበው በፍቅርና በሐሴት የወቅቱ መታሰቢያ የኾነውን የሻደይን በዓል ያከብራ፡፡

እናቶችና እኅቶች በዐደባባይ ወጥተው የድንግል ማርያምን ትንሣኤና ዕርገት እንደ ነጻነታቸው ቀን በመቍጠር ከበሮ አዘጋጅተው ‹‹አሸንድዬ›› የተባለውን ቄጠማ በወገባቸው ታጥቀው ምስጋና በማቅረብ በዓሉን ይዘክራሉ፡፡

በአጠቃላይ የሻደይ ጨዋታ የፍልሰታ በዓል መከበር ከጀመረበት ጊዜ አንሥቶ በምእመኑ ዘንድ ለበርካታ ዓመታት እየተከበረ የኖረ ሃይማኖታዊ በዓል ነው፡፡ ይህንን ሃይማኖታዊ መሠረትነት ያለውን ትውፊት የመጠበቅና የማስጠበቅ ሓላፊነት ከኹላችንም ይጠበቃል። የእመቤታችን አማላጅነት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

‹‹አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፤ አንተና የመቅደስህ ታቦትም›› /መዝ.፻፴፩፥፰/

ነሐሴ ፲፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በመ/ ሳሙኤል ተስፋዬ

St.Marry

የእመቤታችንን መቀብርና ከሞት ተነሥታ ማረጓን የሚሳይ ሥዕል

እግዚአብሔር አምላካችን ‹‹አምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ ስደትህን በስደቴ፣ ሞትህን በሞቴ አጥፍቼ፤ የቀደመ ክብርህን መልሼ ያጣኸውን ርስት፣ ገነትን (መንግሥተ ሰማያትን) አወርስሃለሁ›› በማለት ለአባታችን አዳም የገባው ቃል ኪዳን /ገላ.፬፥፬/ ፍጻሜው በደረሰ ጊዜ ለእግዚአብሔር ወልድ ማደሪያነት የተመረጠች፣ ለአዳም እና ለዘሩ መዳን ምክንያት የኾነች ‹‹የልጅ ልጅ›› የተባለችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዳ ፲፭ ዓመት ሲኾናት በቅዱስ ገብርኤል ብሥራት የእግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ ማደሪያ ኾነች፡፡ ልጇን በወለደች ወቅት የሰብአ ሰገልን ‹‹የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት አለ›› የሚለውን ዜና የሰማ ሄሮድስ ሕፃኑን ለመግደል ዐዋጅ ዐወጀ፡፡ እመቤታችንም ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስን ለማዳን ወደ ግብጽ ይዛው ተሰደደች /ማቴ.፪፥፲፪/፡፡

የስደቱ ዘመን አልቆ ወደ ኢየሩሳሌም ከተመለሱ በኋላም ኢየሱስ ክርስቶስ ፴ ዓመት ሲኾነው ስለ መንግሥተ ሰማያትና ስለ ሰው ልጆች ነጻነት ይሰብክ ጀመር፡፡ ከዚህ በኋላ የአዳምና የዘሩን ሞት ለማጥፋት በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ሞተ፤ በሦስተኛው ቀን ተነሥቶ፣ ባርነትን አስወግዶ ለሰው ልጅ ነጻነትን ዐወጀ፡፡

በዚህ ኹሉ የድኅነት ጉዞ ውስጥ ያልተለየችና ምክንያተ ድኂን የኾነችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደች በ፷፬ ዓመቷ ጥር ፳፩ ቀን ዐርፋለች፡፡ ይህን የእመቤታችን ሞት የሚያስደንቅ መኾኑን ታላቁ የቤተ ክርስቲያናችን አባት ቅዱስ ያሬድ «ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ ሞታ ለማርያም የዐጽብ ለኲሉ፤ ሞት ለማናቸውም ሰው ኹሉ የተገባ ነው፡፡ የማርያም ሞት ግን ኹሉን ያስደንቃል» በማለት ገልጾታል፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት የእመቤታችንን የከበረ ሥጋዋን ገንዘውና ከፍነው ለማሳረፍ ወደ ጌቴሴማኒ መካነ ዕረፍት (የመቃብር ቦታ) ይዘው ሲሔዱ አይሁድ በቅናት መንፈስ ተነሳሥተው «ቀድሞ ልጇን በሦስተኛው ቀን ከሙታን ተነሣ፤ በዐርባኛው ቀን ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ እንደገናም ተመልሶ ይህን ዓለም ለማሳለፍ ይመጣል›› እያሉ ሲያውኩን ይኖራሉ፡፡ አሁን ደግሞ እርሷንም እንደ ልጇ ተነሣች፣ ዐረገች እያሉ ሲያውኩን ሊኖሩ አይደለምን? ኑ! ተሰብሰቡና በእሳት እናቃጥላት» ብለው ተማከሩ፡፡

ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ የከበረ ሥጋዋን የተሸከሙበትን አጎበር (የአልጋ ሸንኮር) በድፍረት ያዘ፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ በእሳት ሰይፍ ሁለት እጆቹን ቆረጣቸው፡፡ እጆቹ ተንጠልጥለው ከቆዩ በኋላ በእውነት የአምላክ እናት ናት በማለት ስለ አመነ እጆቹ ተመልሰው እንደነበሩ ሆነውለታል፡፡ ከዚህ በኋላ መልአከ እግዚአብሔር የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ  ከሐዋርያው ዮሐንስ ጋር ነጥቆ ወስዶ በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አስቀመጠው፡፡

ቅዱስ ዮሐንስም ከጥቂት ጊዜ በኋላ ወደ ሐዋርያት ሲመጣ የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ በገነት መኖሩን ነገራቸው፡፡ ሐዋርያትም የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ አግኝተው  ለመቅበር በነበራቸው ምኞትና ጉጉት ‹‹ዮሐንስ አይቶ እኛ እንዴት ሳናይ እንቀራለን? ብንጠየቅስ ምን እንመልሳለን?›› በማለት በነሐሴ አንድ ቀን ሱባኤ ጀምረው ሲጾሙና ሲጸልዩ ከሰነበቱ በኋላ በሁለተኛው ሱባዔ መጨረሻ (ነሐሴ ፲፬ ቀን) ጌታችን የእመቤታችንን ትኩስ የከበረ ሥጋ አምጥቶ ሰጥቷቸው በታላቅ ዝማሬና ውዳሴ በጌቴሴማኒ ቀብረውታል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ የእመቤታችን የቀብር ሥነ ሥርዐት ሲፈጸም አልነበረምና ከሀገረ ስብከቱ በደመና ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመጣ እመቤታችን በተቀበረች በሦስተኛው ቀን  እንደ ልጇ ተነሥታ ስታርግ አገኛት፡፡ በዚህ ጊዜ ‹‹ቀድሞ የልጅሽን፣ አሁን ደግሞ የአንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ›› ብሎ ቢያዝን እመቤታችን ከእርሱ በቀር ሌሎች ሐዋርያት ትንሣኤዋን እንዳላዩ ነግራ አጽናናችው፡፡ ወደ ምድር ወርዶ የኾነውን ኹሉ ለሐዋርያት እንዲነግራቸው አዝዛው፣ ለምልክት ይኾነው ዘንድም የተገነዘችበትን ሰበኗን ሰጥታው ወደ ሰማይ ዐርጋለች፡፡

ቅዱስ ቶማስም ሐዋርያት ወደ አሉበት ኢየሩሳሌም በደረሰ ጊዜ «የእመቤታችን ነገር እነዴት ኾነ?»  ብሎ ቢጠይቃቸው፤ «እመቤታችንን እኮ ቀበርናት» ብለው ነገሩት፡፡ እርሱም ዐውቆ ምሥጢሩን ደብቆ «አይደረግም ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር  እንደምን ይሆናል?» አላቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ አንተ መጠራጠር ልማድህ ነው፡፡ ቀድሞ የጌታን ትንሣኤ ተጠራጠርክ አሁንም አታምንም›› ብሎ  የእመቤታችን መካነ መቃብር ሊያሳዩት ይዘውት ሔዱ፡፡ መቃብሩን ቢከፍቱ የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ አጡት፤ ደነገጡም፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ቶማስ «አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ተነሥታ ዐርጋለች» ብሎ  የኾነውን ኹሉ ተረከላቸውና የሰጠችውን ሰበኗን አሳያቸው፡፡ እነርሱም ማረጓን አምነው ሰበኗን ለበረከት ከተከፋፈሉ በኋላ ወደየአህጉረ ስብከታቸው ሔዱ፡፡ በየሀገረ ስበከታቸውም ሕሙማንን ሲፈውሱበትና ገቢረ ተአምር ሲያደርጉበት ኖረዋል፡፡

በዓመቱ ‹‹ቶማስ ትንሣኤዋን አይቶ እንዴት እኛ ይቅርብን?›› ብለው ከነሐሴ ፩ ቀን ጀምሮ ሱባዔ ገብተው ነሐሴ ፲፮ ቀን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልመናቸውን ተቀብሎ እመቤታችንን መንበር፣ ቅዱስ ጴጥሮስን ንፍቅ (ረዳት) ቄስ፣ ቅዱስ እስጢፋኖስን ገባሬ ሠናይ (ዋና) ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ አቍርቧቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ እመቤታችንን ሐዋርያት በግልጽ ትንሣኤዋን ዕርገቷን እያዩዋት ከጌታችን ጋር በክብር በይባቤና በዝማሬ ወደ ሰማይ ዐርጋለች፡፡ «እመቤታችን ድንግል ማርያም ከምድር ወደ ሰማይ ዐረገች በሰማይም ከልጇ ጋር በአብና በመንፈስ ቅዱስ ቀኝ ተቀመጠች» እንዳለ ቅዱስ ያሬድ በመዝሙሩ፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት መሠረት ትንሣኤ ጊዜያዊና ዘለዓለማዊ በመባል ይታወቃል፡፡ ጊዜያዊ ትንሣኤ የሚባለው የእግዚአብሔር ከሃሊነት የሚገለጽበት ተአምራዊ ሥራ ኾኖ በተወሰኑ ሰዎች ላይ የሚፈጸምና ዳግም ሞትን የሚያስከትል ነው፡፡ ለምሳሌ ኤልያስ ያስነሣውን ወልደ መበለት /፩ኛነገ. ፲፯፥፰-፳፬/፤ ዐፅመ ኤልሳዕ ያስነሣውን ሰው /፪ኛነገ. ፲፫፥፳-፳፩/፤ ወለተ ኢያኢሮስን /ማቴ.፱፥፰-፳፮/፤ በዕለተ ስቅለት ከመቃብር ወጥተው በቅድስት ከተማ የታዩ ሙታንን /ማቴ. ፳፯፥፶፪-፶፫/፤ በቅዱስ ጴጥሮስ ጸሎትና ምልጃ የተነሣችዋን ጣቢታን /ሐዋ.፱፥፴፮-፵፩/፤ እንደዚሁም ትንሣኤ አልዓዛርን መጥቀስ ይቻላል /ዮሐ.፲፩፥፵፫-፵፬/፡፡ እነዚህ ኹሉ ለጊዜው ከሞት ቢነሡም ቆይተው ግን ተመልሰው ዐርፈዋል፡፡ ወደፊትም ትንሣኤ ዘጉባኤ ይጠብቃቸዋል፡፡

የቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ ግን የክብርና የሕይወት ትንሣኤ ሲኾን ሁለተኛ ሞትን አያስከትልም፤ ትንሣኤ ዘጉባኤንም አይጠብቅም፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤያችን በኵር ኾኖ በሞተ በሦስተኛው  ቀን ተነሥቷል፡፡ እመቤታችንም በልጇ ሥልጣን፤  እንደ ልጇ ትንሣኤ በሦስተኛው ቀን ተነሥታ ትንሣኤ ዘጉባኤን ሳትጠብቅ በክብር ዐርጋለች፡፡  እንደዚህ ያለውን ትንሣኤ ከእርሷ በቀር ሌሎች ቅዱሳን ወይም ነቢያትና ሐዋርያት አላገኙትም፡፡ በዚህም ኹኔታ የቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ ከማናቸውም ትንሣኤ ልዩ ኾኖ እናገኘዋለን፡፡ ይህም ትንሣኤ ዘለዓለማዊ የኾነ ከዳግም ሞተ ሥጋ ነጻ የኾነ ትንሣኤ ነው፡፡

ይህ የእመቤታችን ዕርገት በመጽሐፍ ቅዱስ ከተገለጸው ከእነ ሄኖክና ኤልያስ ዕርገት የተለየ ነው፡፡ «ሄኖክ ሞትን እንዳያይ በእምነት ተወሰደ፤ እግዚአብሔርም ስለ ወሰደው አልተገኘም» ተብሎ እንደ ተጸፈ /ዕብ ፲፩፥፭/፣ ሄኖክ ወደ ሰማይ ያረገው በምድር ሳለ እግዚአብሔርን በእምነቱና በመልካም ሥራው ስላስደስተና በሥራውም ቅዱስ ኾኖ ስለ ተገኘ ሞትን እንዳያይ ሲኾን ወደፊትም ገና ሞት ይጠብቀዋል፤ ሞቶም ትንሣኤ ዘጉባኤ ያስፈልገዋል፡፡ ነቢዩ ኤልያስም በእሳት ሠረገላም ቢነጠቅም /፪ኛነገ.፪፥፲/ ወደፊት ሞት ይጠብቀዋል፤ ትንሣኤ ዘጉባኤም ያስፈልገዋል፡፡

ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት በትንቢቱ «ተንሥእ እግዚኦ ውስተ ዕረፍትከ አንተ ወታቦተ መቅድስከ፤ አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፤ አንተና የመቅደስህ ታቦትም» /መዝ.፻፴፩፥፰/ በማለት አስቀድሞ የክርስቶስን ትንሣኤ ከገለጸ በኋላ ቀጥሎ የመቅደሱ ታቦት እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም ከሞት እንደምትነሣ ተናግሯል /ማቴ.፭፥፴፭፤ ገላ.፬፥፳፮፤ ዕብ. ፲፪፥፳፪፤ ራእ.፫፥፲፪/፡፡

ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ በድርሰቱ ‹‹በቃልዋ የታመነች፣ በሥራዋም የተወደደች ቅድስት ድንግል ማርያምን መላእክት እያመሰገኗትና በመንፈሳዊ ደስታ እያጀቧት ወደ ሰማይ አሳረጓት›› ሲል እንደ ገለጸው፣ በመጽሐፈ ስንክሳርም እንደ ተመዘገበው ቅዱስ ዳዊት ‹‹በወርቅ ልብስ ተጐናጽፋ፣ ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች›› /መዝ.፵፬፥፱/ በማለት የተናገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ አባቷ ዳዊት በበገና፣ ነቢዩ ዕዝራ በመሰንቆው እያመሰገኗት፤ በቅዱሳን መላእክት፣ በቅዱሳን ነቢያትና ጻድቃን ዝማሬ በብሩህ ደመና ወደ ሰማይ ዐርጋ በክብር ተቀምጣለች፡፡ በዚያም ሥፍራ ሁለተኛ ሞት ወይም ኀዘን፣ ጩኸትና፣ ስቃይ የለም፡፡ የቀደመው ሥርዐት አልፏልና /ራእ.፳፩፥፬-፭/፡፡

ስለዚህም የእመቤታችን ዕረፍቷ፣ ትንሣኤዋና ዕርገቷ በሚታሰብበት በጾመ ፍልሰታ ሳምንታት ምእመናንን ከአካባቢያቸው ራቅ ብለው በተለያዩ ገዳማትና አድባራት በመሔድ አለዚያም በየአጥቢያቸው በመሰባሰብ እመቤታችን በተለያዩ ጊዜያት ሞቷንና ትንሣኤዋን ለሐዋርያት የገለጸችበትን ኹኔታ ያስባሉ፡፡ በጾም በጸሎት ተወስነው የልጇን ቸርነት የድንግልን አማላጅነት በእምነት ኾነው ይማጸናሉ፡፡ እንደዚሁም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነሐሴ ፲፮ ቀን እናቱን መንበር፣ ቅዱስ ጴጥሮስን ተራዳዒ ካህን፣ ቅዱስ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ ሐዋርያትንም እመቤታችንንም ማቍረቡን በመዘከር ቅዱስ ሥጋውን፣ ክቡር ደሙን ይቀበላሉ፡፡ ሱባዔው ሲፈጸምም «በእውነት ተነሥታለች» እያሉ በደስታ የጾሙን ወቅት ይፈጽማሉ፡፡

የእመቤታችን አማላጅነት፣ የትንሣኤያችን በኲር የኾነው የአምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቸርነት ከኹላችን ጋር ይኹን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

አስደናቂው የድንግል ማርያም ሞትና ትንሣኤ

ነሐሴ ፲፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ታደለ ፈንታው

St.Merry

እመቤታችን ከሙታን ተነሥታ በክብር እንዳረገች የሚያሳይ ሥዕል

በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ የጌታ ልደቱና ጥምቀቱ፣ ሞቱ፣ ትንሣኤው፣ ዕርገቱና ዳግመኛ መምጣቱ በነገረ ድኅነት ትምህርታችን እጅግ ጠቃሚ የኾኑ ምሥጢራት ናቸው፡፡ ቤተልሔም የሥጋዌውን ምሥጢር ሲያሳይ ዮርዳኖስ ቀዳማዊ ልደቱን ያሳያል፡፡ የመጀመርያው የእኛ ባሕርይ ሲኾን ሁለተኛው የጌታ የራሱ የባሕርይ ገንዘቡ የኾነ ነው፡፡ እርሱ የሰው ልጅ ኾነ፤ እኛ ደግሞ የእግዚአብሔር ልጆች ኾንን፡፡ ይህ ኹሉ የተደረገው ከድንግል ማርያም በነሳው ሥጋ ነው፡፡ እርሱ የእኛን ተፈጠሮ ገንዘቡ ስላደረገ፤ እኛ ደግሞ የእርሱን ቅድስና ገንዘብ በማድረግ የመንግሥቱ ተካፋዮች ለመኾን በቃን፡፡ በእርሷ ምክንያት የእኛ የኾነው ኹሉ የእግዚአብሔር፤ የእግዚአብሔር የኾነው የእኛ ኾኗል፡፡ ስለዚህም እግዚአብሔርን ከፍ ከፍ እናደርገዋለን፤ ለዚህ ክብር በቅታ ያከበረችንን፣ ከእግዚአብሔር ጋር ያዛመደችንን እመቤታችንንም እናከብራታለን፡፡

እርስዋ ከኪሩቤል ትበልጣለች፤ ከሱራፌልም ትከብራለች፡፡ ጌታችን የሱራፌልን፣ የኪሩቤልን ባሕርይ ባሕርዩ አላደረገም፡፡ የመላእክትንም ባሕርይ እንደዚሁ፤ የእርሷን አካል ባሕርዩ አደረገ እንጂ፡፡ የእኛ መንፈሳዊ ልደት የተገኘው ጌታ በሥጋ ከቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደው ልደት ነው፡፡ የቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን አምላክና የሰው ልጆች የተገናኙበት፤ አምላክና ሰው የተዋሐዱበት መካነ ምሕረት ነው፡፡ እግዚአብሔር ዙፋኑን ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀናት የዘረጋበት መካነ ሰላም ነው፡፡ የእግዚአብሔር ዙፋን ፍጹም በማይናወጥና ጸጥታ በነገሠበት ሥፍራ የሚዘረጋ የክብር ዙፋን ነው፡፡ ይህም ዙፋን የቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን ነው፡፡

ድንግል ማርያም በአባት በእናቷ ቤት ሦስት ዓመት፤ በቤተ መቅደስ ዐሥራ ሁለት ዓመት፤ ከልጇ ጋር ሠላሳ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር፤ ከጌታችን ስቅለት በኋላ ደግሞ ዐሥራ አምስት ዓመታት በምድር ኖራለች፡፡ ጌታን የፀነሰችበትን ወራት ስንጨምር በዚህ ዓለም በሥጋ የቆየችበት ጊዜ ስድሳ አራት ዓመት ይሆናል፡፡ ኢትዮጵያዊው ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ በመጽሐፈ አርጋኖን ድርሰቱ ‹‹ከሚያሰጥመው ባሕር ሞገድ የተነሣ የማትነቀነቅ፣ መልኅቆቿም በሦስቱ ሥላሴ ገመድ የተሸረቡ ናቸው ይህቺ ደግሞ ከነፋሳት ኃይል የተነሣ የማትናወጥ በጭንጫ ላይ ያለች የዕንቈ ባሕርይ ምሰሶ ናት፤ እርሷን የተጠጋ መውደቅ መሰናከል የለበትም›› የሚላት እመቤታችን ሞት አይቀርምና እርሷም እንደሰው የምትሞትበት ጊዜ ደርሶ ጥር ሃያ አንድ ቀን ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ ዐርፋለች፡፡ እግዚአብሔር አያደላምና /ሮሜ.፪፥፲፩/፡፡

ቅድስት ድንግል ማርያም የኃያሉ እግዚአብሔር እናቱ፣ መቅደሱ፣ ታቦቱ፣ መንበሩ ኾና እያለ ሞትን መቅመሷ በራሱ የሚያስገርም ምሥጢር ነው፡፡ የዚህ ከኅሊናት ኹሉ በላይ የኾነው የእመቤታችን ዕረፍትም እንዲህ ተብሎ ተገልጿል፤ ‹‹ለምንት ይዜኃር ኃያል በኃይሉ ወባዕል በብዝኃ ብዕሉ ኢያድለወ ሞተ ክርስቶስ ለሥጋ አባሉ ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ ሞታ ለማርያም የዐጽብ ለኵሉ፡፡ ኃይለኛ በኃይሉ ለምን ይታጀራል? ባለ ጸጋም በሀብቱ ብዛት፡፡ ክርስቶስ ለአካሉ አላደላም፡፡ ሞትስ ለሟች ይገባዋል፤ የእመቤታችን የቅድስት ማርያም ሞት ግን አስደናቂ ነው›› /መጽሐፈ ዚቅ/፡፡

ጠቢቡ ሰሎሞን እንዲህ አለ፤ ‹‹ወዳጄ ሆይ ተነሺ፤ ውበቴ ሆይ ነይ፡፡ እነሆ ክረምት አለፈ፤ ዝናሙም አልፎ ሔደ፡፡ አበቦች በምድር ላይ ተገለጡ፤ የዜማም ጊዜ ደረሰ፡፡ የቍርዬም ቃል በምድር ላይ ተሰማ፤›› /መኃ.፪፥፲-፲፬/፡፡ ይህ ትንቢት የዚህ ዓለም ድካሟ ኹሉ መፈጸሙን ያስረዳል፡፡ ልጇን ይዛ ከአገር ወደ አገር በረሀብና ጥም የተንከራተተችበት ጊዜ አሁን አለፈ፡፡ ታናሽ ብላቴና ሳለች ልጇን አዝላ በግብጽ በረሃ የተቀበለችው መከራ ኹሉ ፍጻሜ አገኘ፡፡ ከእግረ መስቀል ሥር ወድቃ የልጇን የቈሰለ ገላ እየተመለከተች የደረሰባት ልብ የሚሰነጥቅ ኀዘን ወደ ደስታ ተለወጠ፡፡ ‹‹በነፍሷ ሰይፍ ያልፋል›› ተብሎ የተነገረው ልብ የሚሰነጥቅ መከራ እንደ ነቢዩ ቃል ትንቢት የሚቀጥልበት ጊዜ ተፈጸመ፡፡

የቤተ ክርስቲያን ትውፊት የድንግል ማርያም ሞት በሚከተሉት ምክንያቶች እንደ ኾነ ያስረዳል፤ የመጀመሪያው ‹‹ለመለኮት ማደርያ ለመኾን የበቃችው ኃይል አርያማዊት ብትኾን ነው እንጂ እንደ ምድራዊት ሴትማ እንደምን ሰማይና ምድር የማይችለውን አምላክ ልትሸከመው ይቻላታል?›› የሚሉ ወገኖች ነበሩና እግዚአብሔር ወልድ የተዋሐደው የሰው ልጆችን ሥጋ መኾኑን ለማጠየቅ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን ሲያስረዳ ‹‹እንግዲህ ልጆቹ በሥጋና በደም ስለሚካፈሉ፣ እርሱ ደግሞ በሞት ላይ ሥልጣን ያለውን በሞት እንዲሽር፣ ይኸውም ዲያብሎስ ነው፡፡ በሕይወታቸው ኹሉ ስለሞት ፍርሃት በባርነት ይታሠሩ የነበሩትን ኹሉ ነጻ እንዲያወጣ፣ በሥጋና በደም እንዲሁ ተካፈለ፡፡ የአብርሃምን ዘር ይዟል እንጂ የያዘው የመላእክትን አይደለም›› አለ /ዕብ.፪፥፲፬-፲፭/፡፡ በዚህም ድንግል ማርያም የአዳም ዘር መኾኗ ታወቀ፡፡ ሁለተኛው ቅዱስ ያሬድ እንደተናገረው ጌታችን በፍርዱ አድልዎ የሌለበት መኾኑ ይታወቅ ዘንድ ነው፡፡ ሥጋ የለበሰ ኹሉ ሞትን ይቀምስ ዘንድ የግድ ነውና፡፡

እመቤታችን ባረፈች ጊዜ ሐዋርያት ሊቀብሯት ሲሹም ከአይሁድ ክፋት የተነሣ ልጇ ሌላ ክብርን ደረበላት፡፡ ከጌቴሴማኒ ሥጋዋ ተነጥቆ በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር እስከ ነሐሴ ዐሥራ ስድስት ቀን ለሁለት መቶ አምስት ቀናት ቆይታለች፡፡ ልጇ ወዳጇ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን በሥልጣኑ እንዳሸነፈ የልጇ መለኮታዊ ኃይል ሞትን አሸንፋ እንድትነሣ አደረጋት፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን ስለ ትንሣኤዋ የተናገረው ቃል ተፈጸመ፡፡ ሊቁ ‹‹ለዛቲ ብእሲት ሠረቀ ላዕሌሃ ብዕለ ጸጋሁ ለአብ ወአግዓዛ እምእኩይ ውስተ ሠናይ እሞት ውስተ ሕይወት፤ በድንግል ማርያም ላይ የአብ የባለጸግነቱ ብዛት ተገለጠ፡፡ ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከክፉ ዓለም ወደ በጎ ዓለም አሸጋግሯታልና›› ሲል የተነጋረውም ይኼንን ምሥጢር የሚገልጽ ነው፡፡

ለአምላካችን ለልዑል እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይግባውና ከሞት ወጥመድ በላይ እንኳን የኾነ ሌላ ኃይል አለ፤ ይኼውም ሞት ፈጽሞ ሊያሸንፈውና ሊገዳደረው የማይችል የእግዚአብሔር መለኮታዊ ኃይል ነው፡፡ ሕያው የኾነው እግዚአብሔር የሕያዋን አምላክ ነውና ሞት ሊያሸንፈው፣ ሊደርስበትም የማይችለውን ሕይወት ይሰጣል፡፡ ይህንን እርሱ የሚሰጠውን ሕይወት ሰይጣን በእጁ ሊነካው ከቶውንም አይችልም፡፡ ከሞት ሥልጣንና ኃይል በላይ የኾነው ይኸው የእግዚአብሔር መለኮታዊ ሥልጣን የድንግል ማርያምን ሥጋ ለፍርድ እስከሚመጣበት ጊዜ ድረስ በመቃብር ውስጥ ተጠብቆ እንዲቆይ፤ ፈርሶና በስብሶ በምድር ላይ እንዲቀር አላደረገም፡፡ ከሙታን መካከል ተለይታ ተነሥታለች፡፡ እንድትነሣም ያደረገ የእግዚአብሔር ኃይል ነው እንጂ በራሷ ሥልጣን የተነሣች አይደለችም፡፡ መንፈስ ቅዱስ በድንግልና ፀንሳ በድንግልና መውለዷን በትንቢት እንዳናገረ ትንሣኤዋንም በትንቢት ሲያናግር ኖሯልና ይህ ታላቅ ምሥጢር በቅዱስ ዳዊት አንደበት ‹‹ተንሥእ እግዚኦ ውስተ ዕረፍትከ አንተ ወታቦተ መቅደስከ፤ አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፤ አንተና የመቅደስህ ታቦትም›› ተብሎ ተገልጿል /መዝ.፻፴፩፥፰/፡፡

ቅዱስ ዳዊት በዚህ የትንቢት ክፍል ትንሣኤዋን አስረድቷል፡፡ ታቦት የጽላቱ ማደሪያ ነው፡፡ በታቦቱ ውስጥ የሚያድረው በእግዚአብሔር ጣቶች የተጻፈው ሕጉ ነው፡፡ ይህ እግዚአብሔር ያከበረው ነገር ኾኖ ሊመጣ ላለው ነገር ማሳያ ነው፡፡ እውነተኛዋ ታቦት ማርያም ናት፡፡ ሙሴ በተቀበለው ታቦት ውስጥ ያለው ጽላት በውስጡ የያዘው ሕጉን ነው፤ በድንግል ማርያም ላይ ያደረው ግን የሕጉ ባለቤት ነውና፡፡ ከፍጡራን ከፍ ከፍ የማለቷ ድንቅ ምሥጢርም ይህ ነውና፡፡ የእመቤታችን ትምክህቷም፣ ትውክልቷም ጌታ እግዚአብሔር እንደ ኾነ ወንጌላውያኑ በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝተው መስክረውላታል፡፡ እርሷም ‹‹ነፍሴ እግዚአብሔርን ታከብረዋለች፤ መንፈሴም በአምላኬ፣ በመድኃኒቴ ሐሤትን ታደርጋለች›› በማለት ተናግራለች /ሉቃ.፩፥፵፯/፡፡

እመቤታችን ባለችበት ሥፍራ የሕይወት ትንሣኤ ያላቸው ሰዎች ይኾኑ ዘንድ አስቀድማ ከሙታን ተለይታ በመነሣት የተጠበቀልን ተስፋ ማሳያ ኾነችን፡፡ ከእንግዲህ በኋላ ልጇ ሲንገላታ፣ ሲሰደድ፣ ሲገረፍ፣ ሲሰቀል፣ ሲቸነከር ያየችበት ዓለም አለፈ፡፡ አሁን የልጇን ልዕልና ከሚያደንቁ ጋር ታደንቃለች፤ ከፍ ከፍ ከሚያደርጉት ጋር ታከብረዋለች፡፡ ይኸውም ከገቡ የማይወጡበት፤ ኀዘን፣ መከራ፣ ችግር የሌለበት ሰማያዊ አገር ነው፡፡ በእግዚአብሔር መንግሥት ስደት፣ መከራ፣ ኀዘን፣ ሰቆቃ፣ መገፋት፣ መግፋትም የለም፡፡ ቅዱሳን ሩጫቸውን ጨርሰው የድል አክሊልን የሚቀዳጁበት ሥፍራ ነው፡፡ በዚህም ከፍጡራን ኹሉ ከፍ ባለ በታላቅ ክብርና ጸጋ ለዘለዓለም እንደምትኖር እናምናለን፡፡ ልመናዋ፣ ክብሯ፣ ፍቅሯ፣ አማላጅነቷ፣ የልጇም ቸርነት በኹላችን ላይ አድሮ ይኑር፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡ሐመር ፲፰ ዓመት፣ ቍጥር

ደብረ ታቦርና ቡሄ

ነሐሴ ፲፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ታቦር ብርሃነ መለኮቱን፣ ክብረ መንግሥቱን መግለጡን በማሰብ በየዓመቱ ነሐሴ ፲፫ ቀን በዓሉ ይከበራል፡፡ ይህ በዓል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ዘንድ ‹‹ቡሄ›› በመባል ይታወቃል፡፡

ቡሄ ማለት /መላጣ ፣ ገላጣ/ ማለት ነው፡፡ በአገራችን ክረምቱ፣ አፈናው ተወግዶ የብርሃን ወገግታ የሚታይበት በዚሁ በዓል አካባቢ ስለኾነ ‹‹ቡሄ›› እንደ ተባለ ይገመታል፡፡ ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት፣ ብርሃን የታየበት፣ ድምፀ መለኮት የተሰማበትና ችቦ የሚበራበት ዕለት ስለ ኾነ ደብረ ታቦር የብርሃን ወይም የቡሄ በዓል ይባላል፡፡

ቡሄ ሲመጣ የክረምቱ ጨለማነት አልፎ ወደ ብርሃን፣ ወደ ጥቢ የሚያመራበት፣ ወደ መፀው የሚገባበት፣ ወገግታ የሚታይበት፣ ሰማይ ከጭጋጋማነት ወደ ብሩህነት የሚለወጥበት፣ የሚሸጋገርበት ወቅት በመኾኑ ከቡሄ በኋላ የጠነከረ ክረምት አይኖርም፡፡ ‹‹ቡሄ ከዋለ የለም ክረምት፤ ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት›› እንዲሉ፡፡በአንዳንድ የአገራችን አካባቢዎች የቡሄ ዕለት ማታ ምእመናን ችቦ ያበራሉ፡፡ ይህም በደብረ ታቦር ለታየው ብርሃነ መለኮት ምሳሌ ነው፡፡

ሕፃናቱ ይህ በዓል ከመድረሱ በፊት ቀደም ብለው ጅራፍ ሲገምዱና ሲያጮኹ (ሲያኖጉ) ይሰነብታሉ፡፡ እናቶችም ለዚህ በዓል የሚኾን ዳቦ ለመጋገር ስንዴያቸውን ሲያጥቡ፣ ሲፈትጉ ይሰነብታሉ፡፡ በበዓሉ ዋዜማ (ነሐሴ ፲፪ ቀን) ሕፃናት በየቤቱ እየዞሩ ‹‹ቡሄ ና በሉ፤ ቡሄ በሉ፡፡ ቡሄ መጣ፤ ያ መላጣ፤ ቅቤ ቀቡት እንዳይነጣ፡፡ …›› እያሉ ይጫወታሉ፡፡ ‹‹ቡሄ›› ያሉት ዳቦውን ነው፡፡ በዚህ ጊዜ እናቶች ካዘጋጁት ዳቦ እያነሡ ይሰጧቸዋል፡፡

ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን በገለጠበት ዕለት እረኞች ከብርሃኑ የተነሣ እየተገረሙና እየተደነቁ ወደ ቤት አልተመለሱም ነበር፡፡ የልጆቹን መዘግየት ያዩ ወላጆች ችቦ አብርተውና ዳቦ ይዘው ፍለጋ ወጥተዋል፡፡ «ቡሄ» ለሚሉ ልጆች ሙልሙል ዳቦ የሚሰጠውና ችቦ የሚበራው ከዚህ በመነሣት ነው፡፡ ልጆችም ዳቧቸውን እየገመጡ ጅራፍ ሲገርፉ ይውላሉ፡፡ የጅራፉ መጮኽ የድምፀ መለኮት፣ ጅራፉ ሲጮኽ ማስደንገጡ ነቢያትና ሐዋርያት በድምፀ መለኮት መደንገጣቸውንና መውደቃቸውን ያስታውሳል፡፡

በተጨማሪም ለክርስትና ልጅ፣ ለአማች፣ ለምራት፣ ለዘመድ አዝማድ ኹሉ የቡሄ ዳቦ ይሰጣል፡፡

ደብረ ታቦር ወይም ቡሄ በአብነት ተማሪዎች ‹‹ስለ ደብረ ታቦር›› እያሉ እህል፣ ጌሾ ከምእመናን በመለመንና ገንዘብ በማዋጣት ጠላውን ጠምቀው፣ ዳቦውን ጋግረው፣ ቆሎውን ቆልተው ለደብረ ታቦር ዕለት ሊያስቀድሱ የመጡትን ምእመናን በመጋበዝ በታላቅ ድምቀት ያከብራሉ፡፡

መምህረ ሐዋርያት ኢየሱስ ክርስቶስ ሦስቱን ተማሪዎቹን ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ዮሐንስን ይዞ በደብረ ታቦር ምሥጢር መግለጡን በማስታዎስ የአብነት ተማሪዎች ከመምህራቸው ጋር በመኾን በዓለ ደብረ ታቦርን (ቡሄን) ያከብራሉ፤ ስሙን ይጠራሉ፡፡ ይህም እስከ አሁን ድረስ በትምህርት ቤቶች የሚሠራበት ነባር ትውፊት ነው፡፡

ነገር ግን በአንድ አካባቢዎች በተለይ በከተማ ዙሪያ በዓለ ደብረ ታቦር (ቡሄ) ሃይማኖታዊ ትውፊቱን የለቀቀ ይመስላል፡፡ ለዚህም ልጆች የሚጫወቱበት መዝሙር ግጥሙና ዜማው ዓለማዊ መለእክት የሚበዛበት መኾኑ፤ በወቅቱ ችቦ ከማብራት ይልቅ ርችት መተኮሱና በየመጠጥ ቤቱ እየሰከሩ መጮኹ፤ ወዘተ. የበዓሉን መንፈሳዊ ትውፊት ከሚያደበዝዙ ተግባራት መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ ከዚሁ ኹሉ ጋርም በዚህ በዓል ገንዘብ ለመሰብሰብ ብቻ የሚሽቀዳደሙ ነገር ግን የበዓሉን ታሪካዊ አመጣጥ የማያዉቁ ልጆችም ጥቂቶች አይደሉም፡፡

ስለዚህ ወላጆች ለልጆቻቸው የበዓለ ደብረ ታቦርን መንፈሳዊነት፣ የመዝሙሮቹን ያሬዳዊነትና አከባበሩን ከቤተ ክርስቲያን መምህራን በመጠየቅ ማስተማር፤ ልጆችም ከወላጆች ወይም ከመምህራን በመጠየቅ የበዓሉን አከባበር መረዳትና የዚህን በዓል መንፈሳዊ ትውፊት ሳይበረዝ ለትውልድ ማስተላለፍ ተገቢ ነው እንላለን፡፡

በመጨረሻም በቡሄ በዓል ‹‹ድምፅህን ሰማና በብሩህ ደመና፤ የቡሄው ብርሃን ለእኛ በራልን፤ …›› የሚለውንና ይህን የሚመስሉ መንፈሳውያን መዝሙራትን እየዘመሩ በየቤቱ በመዞር የሚያገኙትን ዳቦና ገንዘብ ለነዳያንና ለቤተ ክርስቲያን የሚሰጡ ልጆችን ማበረታታትና አርአያነታቸውን መከተል ይኖርብናል መልእክታችን ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡-

መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ መ/ር አፈወርቅ ተክሌ፤ ፳፻፭ ዓ.ም፣ ገጽ ፫፻፲፭-፫፻፲፯፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ፤ ፳፻፯ ዓ.ም፣ ገጽ ፻፲፩፡፡

ተስእሎተ ቂሣርያ

ነሐሴ ፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፯ ቀን ከሚከበሩ በዓላት መካከል ‹‹ተስእሎተ ቂሣርያ›› አንደኛው ነው፡፡ የቃሉ (ሐረጉ) ትርጕም ‹‹በቂሣርያ አገር የቀረበ ጥያቄ›› ማለት ሲኾን ይኸውም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ሰዎች ማን ይሉኛል?›› ብሎ ደቀ መዛሙርቱን መጠየቁን ያስረዳል፡፡

በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈው ጌታችን በቂሣርያ አውራጃ ሐዋርያቱን ሰብስቦ ‹‹ሰዎች የሰውን ልጅ (ኢየሱስ ክርስቶስን) ማን ይሉታል?›› ብሎ ሲጠይቃቸው እነርሱም ‹‹ዮሐንስ፣ ኤልያስ፣ ኤርምያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው ይላሉ›› የሚል ምላሽ ሰጥተውታል፡፡ እርሱም መልሶ ‹‹እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ?›› የሚል ጥያቄ ባቀረበላቸው ጊዜ የሐዋርያት አለቃ ቅዱስ ጴጥሮስ ሐዋርያቱን ወክሎ ‹‹አንተ ውእቱ ክርስቶስ ወልደ እግዚአብሔር ሕያው፤ አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ›› ብሎ የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት የሚያስረዳ ምላሽ ሰጥቷል፡፡

የቅዱስ ጴጥሮስ ምላሽም ሰዎች ስለ ክርስቶስ ማንነት ከሚሰጡት ግምትና ከሐዋርያት ዕውቀት በላይ በመኾኑ ጌታችን ‹‹የእኔን አምላክነት ሰማያዊ አባቴ ገለጸልህ እንጂ ሥጋዊ ደማዊ አእምሮ አልገለጸልህም›› በማለት አድንቆለታል፡፡ ከዚህ በኋላ ‹‹አንተ አለት ነህ፤ በአንተ መሠረትነት ቤተ ክርስቲያኔን እሠራታለሁ፡፡ የገሃነም ደጆች (አጋንንት) አይችሏትም፡፡ የመንግሥተ ሰማያትን መክፈቻ እሰጥሃለሁ፡፡ በምድር ያሠርኸው በሰማይም የታሠረ፤ በምድር የፈታኸው በሰማይም የተፈታ ይኾናል›› በማለት ለስብከተ ወንጌል መስፋፋት፣ ለቤተ ክርስቲያናችን መታነፅ፣ ለምእመናን ድኅነት ምክንያት የኾነውን መዓርገ ክህነት ሰጥቶታል /ማቴ.፲፮፥፲፫-፲፱/፡፡

ይህም ሥልጣነ ክህነት በቅዱስ ጴጥሮስ አንጻር ከሐዋርያት ጀምሮ ለሚነሡ አባቶች ካህናት የተሰጠ ሰማያዊ ሀብት ነው፡፡ ዛሬ ምእመናን በኀጢአት ስንሰናከል ከካህናት ፊት ቀርበን የምንናዘዘውና ንስሐ የምንቀበለው፣ እንደዚሁም እየተባረክን ‹‹ይፍቱኝ›› የምንለው ጌታችን ለእነርሱ የሰጣቸውን ሥልጣነ ክህነት መሠረት በማድረግ ነው፡፡ ካህናትም ‹‹ይኅድግ ይፍታሕ ያንጽሕ ወይቀድስ …›› እያሉ ከናዘዙን በኋላ ‹‹እግዚአብሔር ይፍታ›› የሚሉን ከባለቤቱ የማሠር የመፍታት ሥልጣን ስለ ተሰጣቸው ነው፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰዎች ስለ እርሱ የሚናገሩትንም፣ የሚያስቡትንም የሚያውቅ አምላክ ሲኾን በቂሣርያ ሐዋርያቱን ‹‹ሰዎች ማን ይሉኛል›› ብሎ መጠየቁ በአንድ በኩል አላዋቂ ሥጋን መልበሱን ለማጠየቅ፤ በሌላ ምሥጢር ደግሞ ሐዋርያቱን ‹‹እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ›› ብሎ በመጠየቅ አምላክ ወልደ አምላክ መኾኑን ለመግለጥና መዓርገ ክህነትን ለሐዋርያትና ለተከታዮቻቸው (ለጳጳሳት፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት) ለመስጠት ነው፡፡ ይህም በቅዱስ ጴጥሮስ ምላሽና ጌታችን ለጴጥሮስ በሰጠው ሥልጣን ይታወቃል፡፡

በዚህ በተስእሎተ ቂሣርያ ጌታችን ሐዋርያቱ ማን እንደሚሉት ስለ ማንነቱ ከጠየቃቸው በኋላ ምላሻቸውን ተከትሎ ሥልጣነ ክህነትን መስጠቱ በብሉይ ኪዳን (እግዚአብሔር በሥጋ ከመገለጡ በፊት) አዳም የት እንዳለ እያወቀ ‹‹አዳም ሆይ ወዴት ነህ?›› /ዘፍ.፫፥፲/ ብሎ ከጠየቀውና ያለበትን እንዲናገር ካደረገው በኋላ ‹‹ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ›› የሚል የድኅንት ቃል ኪዳን መግባቱን ያስታውሰናል /ቀሌምንጦስ/፡፡

እንደዚሁም እግዚአብሔር በሦስትነቱ ከአብርሃም ቤት በገባ ጊዜ ሣራ ያለችበትን ቦታ እያወቀ አብርሃምን ‹‹ሚስትህ ሣራ ወዴት ናት?›› ሲል ያለችበትን ቦታ ካናገረው በኋላ ‹‹ሣራ የዛሬ ዓመት ልጅን ታገኛለች›› የሚል በአንድ በኩል የይስሐቅን መወለድ፤ በሌላ በኩል ደግሞ የእግዚአብሔርን ሰው መኾንና የሐዲስ ኪዳንን መመሥረት የሚያበሥር ቃል መናገሩ ከዚህ ትምህርት ጋር ተመሳሳይነት አለው /ዘፍ.፲፰፥፱-፲፭/፡፡

በሐዲስ ኪዳንም አልዓዛር በሞተ ጊዜ የተቀበረበትን ቦታ እያወቀ ‹‹አልዓዛርን ወዴት ቀበራችሁት›› /ዮሐ.፲፩፥፴፯/ ብሎ መካነ መቃብሩን ከጠየቀ በኋላ በሥልጣኑ ከሞት እንዲነሣ ማድረጉም ከተስእሎተ ቂሣርያ ጋርና ከላይ ከጠቀስናቸው ምሳሌዎች ጋር የሚወራረስ ምሥጢር አለው፡፡ ይኼ ኹሉ ቃል እግዚአብሔር ያላወቀ መስሎ እየጠየቀ ሰዎች ስሜታቸውን እንዲገልጡ በማድረግ የልባቸውን መሻትና እምነት መሠረት አድርጎ ሥልጣንን፣ በረከትን፣ ጸጋንና ፈውስን እንደሚያድል የሚያስረዳ ትምህርት ነው፡፡ ለዚህም ጌታችን በመዋዕለ ሥጋዌው በምድር በአካለ ሥጋ ሲመላለስ መዳን እንደሚፈልጉ እያወቀ ‹‹ልትድን ትወዳለህን? (ልትድኚ ትወጃለሽን?) ብሎ እየጠየቀ የልባቸውን መሻት እንዲናገሩ ካደረገ በኋላ እምነታቸውን አይቶ በአምላካዊ ቃሉ ‹‹ፈቀድኩ ንጻሕ /ንጽሒ፤ ፈቅጃለሁ ተፈወስ /ተፈወሺ›› እያለ ለሕሙማነ ሥጋ ወነፍስ ፈውስን ማደሉ ትልቅ ማስረጃ ነው፡፡

የእያንዳንዳችንን የልብ መሻት የሚያውቅ አምላክ እኛንም በቸርነቱ ከደዌ ሥጋ ወነፍስ እንዲፈውሰን ቅዱስ ፈቃዱ ይኹንልን፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ፅንሰተ ማርያም ድንግል

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ ‹‹ቀደሰ ማኅደሮ ልዑል …፤ ልዑል እግዚአብሔር ማደሪያውን መረጠ፤ አከበረ፤ ለየ፤ ቀደሰ …›› /መዝ.፵፭፥፬/ በማለት እንደተናገረው፣ አምላክን በማኅፀኗ ለመሸከም የተመረጠችው ማኅደረ ማለኮት፤ የዓለሙን ቤዛ በመውለዷ ‹‹ቤዛዊተ ዓለም›› እየተባለች የምትጠራው፤ በአምላክ ሕሊና ታስባ ትኖር የነበረችው የድኅነታችን ምክንያት የኾነችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በማኅፀን የተቋጠረችው ነሐሴ ፯ ቀን ነው፡፡ ፅንሰቷም እግዚአብሔር በባረከውና ባከበረው ቅዱስ ጋብቻ በተወሰኑት ወላጆቿ በቅዱስ ኢያቄምና በቅድስት ሐና ሥርዓት ያለው ግንኙነት አማካይነት ነው፡፡ ‹‹ኦ ድንግል አኮ በፍትወተ ደነስ ዘተፀነስኪ አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ፤ ድንግል ሆይ በሥጋዊ ፈቃድ የተፀንሽ አይደለሽም፤ ሕጋዊ በኾነ ሥርዓት ከሐና እና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጂ›› እንዲል /ቅዳሴ ማርያም/፡፡

ታሪኩን ለማስታዎስ ያህል የእመቤታችን ቅድመ አያቶቿ ቴክታ እና በጥሪቃ ይህ ቀራቸው የማይባሉ ባለጠጎች እና መካኖች ነበሩ፡፡ በጥሪቃ ሚስቱ ቴክታን ‹‹አንቺ መካን፤ እኔ መካን፡፡ ይህ ኹሉ ገንዘብ ለማን ይኾናል?›› አላት፡፡ ቴክታም ‹‹እግዚአብሔር ከእኔ ልጅ ባይሰጥህ ከሌላ ይሰጥህ ይኾናል፡፡ ሌላ ሚስት አግብተህ ልጅ አትወልድምን?›› ብትለው ‹‹ይህንስ እንዳላደርገው አምላከ እስራኤል ያውቃል›› አላት፡፡ ኹለቱም እያዘኑ ሲኖሩ አንድ ቀን ነጭ እንቦሳ (ጥጃ) ከበረታቸው ስትወጣ፤ እንቦሳይቱ እንቦሳ እየወለደች እስከ ስድስት ልጅ ስትደርስና ስድስተኛዪቱ እንቦሳም ጨረቃን፣ ጨረቃም ፀሐይን ስትወልድ ራእይ አዩ፡፡

ራእያቸውን ለሕልም ተርጓሚ ሲነግሩም ‹‹የጨረቃዪቱ ትርጕም ከፍጡራን በላይ የምትኾን ልጅ እንደምታገኙ የሚያመለክት ነው፡፡ የፀሐይ ነገር ግን አልተገለጠልኝም፡፡ እንደ ነቢይ፣ እንደ ንጉሥ ያለ ይኾናል፤›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹ጊዜ ይተርጕመው ብለው›› ወደ ቤታቸው ከተመለሱ በኋላ ቴክታ ሴት ልጅ ወለደች፤ ስሟንም ሄኤሜን አለቻት፡፡ ትርጕሙም ስእለቴን (ምኞቴን) አገኘሁ ማለት ነው፡፡ ሄኤሜን ዴርዴን፤ ዴርዴ ቶናን፤ ቶና ሲካርን፤ ሲካር ሄርሜላን፤ ሄርሜላ ሐናን ወለደች፡፡ ሐና ለዓቅመ ሄዋን ስትደርስም ኢያቄም ለሚባል ደግ ሰው አጋቧት፡፡ እነርሱም እንደ በጥሪቃና ቴክታ መካኖች ነበሩ፡፡ በእስራኤላውያን ባህል መካንነት የእርግማን ምልክት ተደርጎ ይቈጠር ነበርና ሐና እና ኢያቄም ብዙ ዘለፋና ሽሙጥ ይደርስባቸው ነበር፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን መሥዋዕት ለማቅረብ ወደ ቤተ መቅደስ ቢሔዱ የዘመኑ ሊቀ ካህናት ሮቤል መካን መኾናቸውን ያውቅ ነበርና ‹‹እናንተማ ‹ብዙ ተባዙ› ብሎ እግዚአብሔር ለአዳም የነገረውን ያስቀረባችሁ ርጉማን አይደላችሁምን? እግዚአብሔር ቢጠላችሁ እንጂ ቢወዳችሁማ ልጅ ይሰጣችሁ አልነበረምን?›› ብሎ መሥዋዕታቸውን ሳይቀበላቸው በመቅረቱ፤ አንድም ከአዕሩገ እስራኤል (ከአረጋውያን እስራኤላውያን) የተወለዱ ሰዎች የሚመገቡትን ተረፈ መሥዋዕት እንዳይመገቡ በመከልከሉ እያዘኑ ሲመለሱ ከልጆቻቸው ጋር የሚጫወቱ ርግቦችንና አብበው ያፈሩ ዕፀዋትን ሐና ተመለከተች፡፡ እርሷም ‹‹ርግቦችን በባሕርያቸው መራባት እንዲችሉ፤ ዕፀዋትን አብበው እንዲያፈሩ የምታደርግ ጌታ እኔን ለምን ልጅ ነሳኸኝ?›› ብላ አዘነች፡፡

ከቤታቸው ሲደርሱም ‹‹እግዚአብሔር ልጅ ቢሰጠን ወንድ ከኾነ ለቤተ እግዚአብሔር ምንጣፍ አንጣፊ፣ መጋረጃ ጋራጅ ኾኖ ሲያገለግል ይኑር፤ ሴት ብትኾንም መሶበ ወርቅ ሰፍታ፣ መጋረጃ ፈትላ ስታገለግል ትኑር›› ብለው ከተሳሉ በኋላ ሐምሌ ፴ ቀን ሐና ለኢያቄም ‹‹በሕልሜ ፀምር (መጋረጃ) ሲያስታጥቁህ፤ በትርህ አፍርታ ፍጥረት ኹሉ ሲመገባት አየሁ›› ብላ ያየቸውን ራእይ ነገረችው፡፡ ኢያቄም ደግሞ ለሐና ‹‹ጸዓዳ ረግብ ሰባቱን ሰማያት ሰንጥቃ መጥታ በራስሽ ላይ ስታርፍ፣ በቀኝ ጆሮሽ ገብታ በማኅፀንሽ ስታድር አየሁ›› ብሎ ያየውን ራእይ ነገራት፡፡ ሕልም ተርጓሚው ‹‹ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ›› ባላቸው ጊዜም ‹‹አንተ አልፈታኸውም፤ ጊዜ ይፍታው›› ብለው ተመልሰዋል፡፡

ከዚህ በኋላ የእግዚአብሔር መልአክ ‹‹ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ›› ብሎ ነግሯቸው ሐዲስ ኪዳን ሊበሠር፤ ጌታችን ሊፀነስ ፲፬ ያህል ዓመታት ሲቀሩ ነሐሴ ፯ ቀን በፈቃደ እግዚአብሔር እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተፀንሳለች፡፡ እመቤታችን በሐና ማኅፀን ውስጥ ሳለች ከተደረጉ ተአምራት መካከልም በርሴባ የምትባል አንድ ዓይና ሴት (አክስቷ) ሐናን ‹‹እግዚአብሔር በረድኤት ጐበኘሽ መሰለኝ ጡቶችሽ ጠቁረዋል፤ ከንፈሮችሽ አረዋል›› ብላ ማኅፀኗን በዳሰሰችበት እጇ ብታሸው ዓይኗ በርቶላታል፡፡ ይህንን አብነት አድርገውም ብዙ ሕሙማን ከደዌያቸው ተፈውሰዋል፡፡

ዳግመኛም ሳምናስ የሚባል ያጎቷ ልጅ በሞተ ጊዜ ሐና የአልጋውን ሸንኮር ይዛ ስታለቅስ ጥላዋ ቢያርፍበት ከሞት ተነሥቶ ‹‹ሰላም ለኪ ኦ እምሔውቱ ለዘገብረ ሰማየ ወምድረ፤ ሰማይና ምድርን የፈጠረው አምላክ አያቱ ሐና ሆይ ሰላም ላንቺ ይኹን›› ብሎ ሕልም ተርጓሚው ያልፈታውን ራእይ በመተርጐም ከሐና እመቤታችን፤ ከእመቤታችን ደግሞ እውነተኛ ፀሐይ የተባለው ክርስቶስ እንሚወለድ አስቀድሞ ተናግሯል፡፡ /ምንጭ፡- ቅዳሴ ማርያም አንድምታ ትርጓሜ፣ ፭፥፴፰/፡፡

በአጠቃላይ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው ‹‹ኦ ማርያም በእንተዝ ናፈቅረኪ ወናዓብየኪ እስመ ወለድኪ ለነ መብልዐ ጽድቅ ዘበአማን ወስቴ ሕይወት ዘበአማን፤ ማርያም ሆይ እውነተኛውን ምግብ፣ እውነተኛውን መጠጥ አስገኝተሽልናልና እናከብርሻለን፤ እናገንሻለን፤›› በማለት እንደ አመሰገናት እኛም ዘለዓለማዊ ሕይወት የሚሰጠውን፤ ከሞተ ሥጋ ከሞተ ነፍስ ማዳን የሚቻለውን፤ እውነተኛውን ምግበ ሥጋ ወነፍስ ኢየሱስ ክርስቶስን ስለወለደችልን ‹‹እናታችን፣ አማላጃችን፣ የድኅነታችን ምክንያት፣ ወዘተ›› እያልን እመቤታችንን እናከብራታለን፤ እናገናታለን፤ እናመሰግናታለን፡፡ እናቱን በአማላጅነት፤ ራሱን በቤዛነት ለሰጠን ለልዑል እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይድረሰው፤ የእመቤታችን በረከት አይለየን፡፡