፫.ጾመ ሐዋርያት እና ጾመ ድኅነት

ሰኔ ፲፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

እንደሚታወቀው በዓለ ጰራቅሊጦስን ተከትለው ሁለት ዐበይት አጽዋማት ይጀመራሉ፡፡ እነዚህም ጾመ ሐዋርያት እና ጾመ ድኅነት (ረቡዕና ዓርብ) ሲኾኑ፣ ቍጥራቸውም ከሰባቱ አጽዋማት ውስጥ ነው፡፡ ስለኾነም ኹላችንም ልንጾማቸው እንደሚገባ በቤተ ክርስቲያን ሕግ ታዝዟል፡፡ ይህም ከቀደሙ አባቶቻችን ጀምሮ የመጣ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሥርዓት እንጂ እንግዳ ሕግ አይደለም፡፡

ቅዱሳት መጻሕፍት እንደሚናገሩት በብሉይ ኪዳን ነቢዩ ሙሴ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቀበለውን ሕገ ኦሪት ለሕዝቡ ከማስተማሩ በፊት ጾሟል /ዘፀ.፴፬፥፳፰/፡፡ ቅዱሳን ነቢያትም የተስፋውን ቃል መፈጸም እየተጠባበቁ እግዚአብሔርን ውረድ፤ ተወለድ እያሉ ይጾሙ፣ ይጸልዩ ነበር፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ጾም የምግባር መሠረት መኾኑን ሊያስተምረን ወንጌልን ከመስበኩ አስቀድሞ ጾሟል /ማቴ.፬፥፩-፲፩/፤ ሐዋርያትም በበዓለ ኀምሳ መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላ ሕገ ወንጌልን ለሕዝቡ ከማስተማራቸው አስቀድሞ ጾመዋል፡፡

እኛም እነርሱን ተከትለን፣ በእነርሱ ሥርዓት በመመራት፣ በሐዋርያት ላይ ያደረው የመንፈስ ቅዱስ ጸጋና ሀብት በእኛም ላይ እንዲያድርብን በየዓመቱ ጾመ ሐዋርያትንና ሌሎችንም አጽዋማት መጾም እንደሚገባን በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ተወስኗል /ፍት.ነገ. ፲፭፥፭፻፹፮/፡፡

ጾመ ድኅነት ስሙ እንደሚያመለክተው የመዳን ጾም ማለት ሲኾን፣ ይህም በብሉይ ኪዳኑ አጽዋማት በጾመ አስቴር እና በጾመ ዮዲት የተተካ የሐዲስ ኪዳን ጾም ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን በሐማ ምክንያት በእስራኤል ላይ ታውጆ የነበረው ሞት በጾመ አስቴር እንደ ተሻረ ኹሉ፣ በሐዲስ ኪዳንም በዕለተ ረቡዕ በጌታችን ላይ በተፈጸመው ምክር የሰይጣን ሴራ ፈርሷልና በጾመ አስቴር ምትክ ረቡዕን እንጾማለን፡፡

እንደዚሁም በብሉይ ኪዳን በጾመ ዮዲት ምክንያት ሆሎሆርኒስ ድል እንደ ተደረገበት ኹሉ፣ በሐዲስ ኪዳንም መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዓርብ በመስቀል ላይ በከፈለው መሥዋዕትነት ዲያብሎስ ድል ተደርጓልና በጾመ ዮዲት ምትክ ዓርብን እንጾማለን፡፡ የእነዚህ የሁለቱ ቀናት (የረቡዕና ዓርብ) ጾም ጾመ ድኅነት ይባላል፡፡

በአጠቃላይ ጾመ ሐዋርያትና ጾመ ድኅነት እንደ ጾመ ነነዌና ዐቢይ ጾም የበዓላትና የአጽዋማት ማውጫ ቀመርን ተከትለው የሚመጡ ከሰባቱ አጽዋማት መካከል የሚመደቡ ጾሞች ናቸው፡፡ የጾመ ሐዋርያት ፋሲካ (መፈጸሚያ) የቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ በዓለ ዕረፍት (ሐምሌ ፭ ቀን) ሲኾን፣ ጾመ ድኅነት ግን ከበዓለ ኀምሳ በስተቀር ዓመቱን ሙሉ የሚጾም ጾም ነው፡፡

ዕለተ ረቡዕ የጌታ ሞት የተመከረበት፤ ዓርብም አምላካችን የተሰቀለበት ዕለት ነውና በመስቀሉ መሥዋዕትነት ያገኘውን ድኅነት ዘወትር ማሰብ ስለሚገባን ሁልጊዜ እንድንጾማቸው በቅዱስ ሲኖዶስ ሥርዓት ተሠርቶልናል፡፡ በዚህ ዓመት ጾመ ሐዋርያት ሰኔ ፲፫፤ ጾመ ድኅነት ደግሞ ሰኔ ፲፭ ቀን ይጀመራሉ፡፡

በመኾኑም የምንጠቀመው በራሳችን መልካም ተግባር፤ የምንወቀሰውም በራሳችን መጥፎ ድርጊት መኾኑን ተረድተን ይኼ የቄሶች፤ ይኼ የመነኰሳት ነው የሚል ሰበብ ሳንፈጥር ኹላችንም በአንድነት ብንጾማቸው ከእግዚአብሔር ዘንድ የምናገኘው ጸጋና ሀብት ይበዛልናልና ራሳችንን ለጾም እናዘጋጅ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የጰራቅሊጦስ መዝሙርና ምንባባት

ሰኔ ፲፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዓለ ጰራቅሊጦስ ከዘጠኙ የጌታችን ዐበይት በዓላት አንዱ ሲኾን በዕለቱ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው የቅዱስ ያሬድ መዝሙርም ይትፌሣሕ የሚለው የትንሣኤ መዝሙር ነው፡፡ እንደ መዝሙሩ ኹሉ በጰራቅሊጦስ በዓል በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የቅዱሳት መጻሕፍት ክፍሎችም በትንሣኤ ዕለት የተነበቡት ምንባባት ናቸው፡፡

እነዚህም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ በመነሣቱ፣ በማረጉና መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት በመላኩ፤ እንደዚሁም ሥጋውን ቈርሶ፣ ደሙን አፍስሶ የሰውን ልጅ ከዘለዓለም ሞት በማዳኑ የሰው ዘር ብቻ ሳይኾን የሰማይ መላእክት፣ የምድር ፍጥረታት ሳይቀሩ ሐሤት እንደሚያደርጉ፤ ምድርም በክርስቶስ ደም በመንጻቷ የጌታችንን ትንሣኤ በደስታ እንደምታከብር ያስረዳሉ፡፡

በበዓለ ጰራቅሊጦስ ውስጥ ባሉት ሰንበታት (እሑዶች) የሚዘመሩ መዝሙራት ትንሣኤን፣ ዕርገትንና የመንፈስ ቅዱስን መውረድ የሚያስረዱ ሲኾኑ፣ ዓላማቸውም ከሙታን ተለይቶ ለተነሣው፣ አዳምና ልጆቹን ከዲያብሎስ ባርነትና ከሲኦል ላወጣቸው ለልዑል እግዚአብሔር ምስጋና ማቅረብ ነው፡፡

እንደ መዝሙሩ ኹሉ በጰራቅሊጦስ በዓል በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የቅዱሳት መጻሕፍት ክፍሎችም በትንሣኤ ዕለት የተነበቡ ምንባባት ሲኾኑ፣ እነዚህም የሚከተሉት ናቸው፤

ከጳውሎስ መልእክታት፡- ፩ኛ ቆሮንቶስ ፲፭፥፳-፵፩፤

ከሌሎች መልእክታት፡- ፩ኛ ጴጥሮስ ፩፥፩-፲፫፤

የሐዋርያት ሥራ ፪፥፳፪-፴፯፤

ምስባክ፡- መዝሙር ፻፲፯፥፳፬፤

ወንጌል፡- ዮሐንስ ፳፥፩-፲፱፤

ቅዳሴ፡- ዲዮስቆሮስ፡፡

በዓለ ጰራቅሊጦስ፣ ጾመ ሐዋርያትና ጾመ ድኅነት

ሰኔ ፲፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች ሰኔ ፲፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በዓለ ጰራቅሊጦስ በሚል ርእስ አቅርበነው የነበረውን ጽሑፍ ለንባብ እንዲያመች በዓለ ጰራቅሊጦስ፣ የጰራቅሊጦስ መዝሙርና ምንባባት፣ እንደዚሁም ጾመ ሐዋርያትና ጾመ ድኅነት በሚሉ ሦስት ንዑሳን አርእስት ከፋፍለን እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

፩.በዓለ ጰራቅሊጦስ

*ጰራቅሊጦስ* የሚለው ቃል ከሦስቱ አካላት አንዱ ለኾነው ለእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ መጠሪያ ስሙ ሲኾን፣ ትርጕሙም በጽርዕ (ግሪክ) ቋንቋ ናዛዚ (የሚናዝዝ)፣ መጽንዒ (የሚያጸና)፣ መስተፍሥሒ (የሚያስደስት) ማለት ነው፡፡ በዓለ ጰራቅሊጦስ በሌላ ቃል በዓለ ጰንጠቆስጤ በመባልም ይታወቃል፡፡ ይኸውም በግሪክ ቋንቋ በዓለ ኀምሳ፣ የፋሲካ ኀምሳኛ ዕለት፣ በዓለ ሠዊት (የእሸት፣ የመከር በዓል) ማለት ነው /ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ ገጽ ፱፻፮ እና ፱፻፯/፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ካረገ በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ፲፪ቱ ደቀ መዛሙርት፣ ፸፪ቱ አርድእት፣ ፭፻ው ባልንጀሮችና ፴፮ቱ ቅዱሳት አንስት በኢሩሳሌም ከተማ በአንድነት ኾነው ለጸሎት ይተጉ ነበር፡፡ በሚያርግበት ጊዜም *እነሆ አባቴ የሰጠውን ተስፋ እኔ እልክላችኋለሁ፤ እናንተ ግን ከላይ ኃይል እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆዩ፤* /ሉቃ. ፳፬፥፵፱/ ሲል ለሐዋርያቱ በገባላቸው ቃል መሠረት ባረገ በ፲ኛው ቀን መንፈስ ቅዱስን ልኮላቸዋል፡፡

በሐዋርያት ሥራ እንደ ተጻፈው በበዓለ ጰራቅሊጦስ ማለዳ ኹሉም በአንድ ቦታ ተሰብስበው ሳሉ እንደ ዐውሎ ነፋስ ያለ ድምፅ ድንገት ከሰማይ መጣና የነበሩበትን ቤት ሞላው፡፡ ከዚያም እንደ እሳት የተከፋፈሉ የእሳት ላንቃዎች በኹሉም ላይ ተቀመጡባቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ኹላቸውም መንፈስ ቅዱስን ከተሞሉ በኋላ መንፈስ ቅዱስ ባደላቸው መጠን በየአገሩ ቋንቋዎች ኹሉ መናገር ጀመሩ /ሐዋ.፪፥፩-፬/፡፡ ጌታችን መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት የላከበት ይህ ዐቢይ በዓል ጰራቅሊጦስ ይባላል፡፡

ጌታችን ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ ከ፶ኛው፤ ከዐረገ ከ፲ኛው ቀን ጀምሮ እስከሚቀጥለው እሑድ ድረስ ያለው ወቅትም ዘመነ ጰራቅሊጦስ ተብሎ የሚጠራ ሲኾን፣ ይህ በዓል ካህናተ ኦሪት ዐሥራቱን፣ በኵራቱን፣ ቀዳምያቱን ይቀበሉበት ነበርና በብሉይ ኪዳን በዓለ ሠዊት ይባል ነበር፡፡ በበዓለ ጰራቅሊጦስም ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ተቀብለውበታልና በበዓለ ሠዊት ምትክ በዓለ ጰራቅሊጦስ ገብቶበታል፡፡

የበዓለ ትንሣኤ መነሻው የአይሁድ የፋሲካ በዓል ማለትም በግብፅ እስራኤል ከሞት የዳኑበት የመታሰቢያ በዓል እንደ ኾነው ኹሉ፣ ለበዓለ ጰራቅሊጦስም መነሻው ይኸው የአይሁድ የፋሲካ በዓል ነው፡፡ የአይሁድ ፋሲካ ከተከበረ ከሰባት ሳምንታት በኋላ በ፶ኛው ቀን የሩቆቹ ከከተሙበት ወጥተው፣ የቅርቦቹ ከተሰባሰቡበት ተገናኝተው ለበዓሉ ፍጻሜ የሚኾነውን በዓለ ሠዊት ያከብሩ ነበር፡፡

ከግብፅ እስከ ከነዓን ምድር የደረሰው የእንስሳት መሥዋዕት ሲጠናቀቅ በ፶ኛው ቀን ይሰባሰብ የነበረው የአይሁድ ጉባኤም መንፈስ ቅዱስ ከወረደበት ዕለት ጀምሮ ተበትኗል፡፡ መሥዋዕተ ኦሪቱ በአማናዊው መሥዋዕት በኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋና ደም እንደ ተለወጠ ኹሉ ጉባኤ አይሁድም በኢየሩሳሌም ከተማ በተሰበሰቡ በቅዱሳን ሐዋርያት ጉባኤ ተለውጧል (ተቀይሯል)፡፡ ይህችውም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ *ከኹሉ በላይ በምትኾን፣ ሐዋርያት በሰበሰቧት በአንዲት፣ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን፤* እንዳሉ ሠለስቱ ምእት /ጸሎተ ሃይማኖት/፡፡

ሐዋርያት በጽርሐ ጽዮን ተሰብስበው ሳሉ መንፈስ ቅዱስ በእሳት አምሳል ወርዶ ሰማያዊ ሀብትን፣ ዕውቀትና ጸጋን አድሏቸዋል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላም በአእምሮ ጎልምሰዋል፤ ጥቡዓን (ቈራጦች)፣ ጽኑዓን ኾነዋል፤ ለስብከተ ወንጌል የሚፋጠኑበትንና ለሰማዕትነት የሚዘጋጁበትን ልቡና ታድለዋል፡፡ ቀድሞ ይናገሩት ከነበሩት ከዕብራይስጥ ቋንቋ በተጨማሪ ፸፩ ቋንቋዎች ተገልጸውላቸው ምሥጢራትን መተርጐም ጀምረዋል፡፡ ሐዋርያት በየገአሩ ቋንቋ ሲናገሩ የሰሙ ከአይሁድ ወገን አንዳንዶቹም ሐዋርያትን *ጉሽ ጠጅ ጠጥተው ሰክረው የኾነ ያልኾነውን ይቀባጥራሉ* ይሏቸው ነበር፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም ይህንን ዐሳባቸውን በመንፈስ ቅዱስ አውቆ *ሰክረዋል የምትሉ እናንተ እንደምትጠራጠሩት አይደለም፡፡ ጊዜው ማለዳ፣ ሰዓቱም ገና ሦስት ሰዓት ነውና፡፡ ዳሩ ግን በነቢዩ ኢዩኤል ከዚህም በኋላ እንዲህ ይሆናል፤ መንፈሴን በሥጋ ለባሽ ሁሉ ላይ አፈስሳለሁ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችሁም ትንቢት ይናገራሉ፤ /ኢዩ.፪፥፳፰/ ተብሎ የተነገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ይህንን ድንቅ ተአምር ያደረገው እናንተ የሰቀላችሁት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤* በማለት ሐዋርያት ኢየሱስ ክርስቶስ ነቢያት ትንቢት የተናገሩለት፣ ምሳሌ የመሰሉለት አምላክ ወልደ አምላክ መኾኑን፣ ከሙታን ተለይቶ መነሣቱን፣ ማረጉንና ዳግም በክብር በምስጋና መጥቶ በሕያዋንና በሙታን ላይ የሚፈረድ መኾኑን እንደሚመሰክሩ በአይሁድ ፊት አሰምቶ ተናገረ፡፡

በቅዱስ ጴጥሮስ ትምህርት የተማረኩ አሕዛብም *ምን እናድርግ* ብለው በጠየቁት ጊዜ ከክፋታቸው ተመልሰው፣ ንስሐ ገብተው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንዲጠመቁ ነገራቸው፡፡ በዚያችም ሰዓት ሦስት ሺህ ሕዝብ በኢየሱስ ክርስቶስ አምኖ ተጠምቋል /ሐዋ.፪፥፩-፵፩/፡፡ ይህም ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላ ያደረባቸው የማሳመን ጸጋና ተአምራትን የማድረግ ኃይላቸው እንደ በዛላቸው ያመላክታል፡፡

ይህ ዕለት ሀብተ መንፈስ ቅዱስ የተሰጠበትና ብዙ ሺሕ ምእመናን የተገኙበት ዕለት በመኾኑ ሊቃውንት የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን በማለት ይጠሩታል፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት *በዚህች ቀን በሦስት ሰዓት ኢየሱስ ክርስቶስ ጰራቅሊጦስን ልኮልናልና በላያችን ኃይልን ሞላ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ በሕያዋንና በሙታን ይፈርድ ዘንድ ሥልጣን እንዳለው በአዲስ ቋንቋ ተናገርን፤* በማለት በዕለቱ ያዩትንና የተደረገላቸውን፣ እንደዚሁም ስለ በዓሉ ታላቅነት ከመሰከሩ በኋላ ይህንን በዓል ማክበር እንደሚገባ አዝዘዋል፤ በአንጻሩ በዚህ ወቅት (በበዓለ ኀምሳ) መጾምና ማዘን ተገቢ አለመኾኑንም ተናግረዋል /ዲድስቅልያ ፴፥፴፰-፴፱፤ ፴፩፥፷፱-፸/፡፡

በዓለ ጰራቅሊጦስ

ሰኔ ፲፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

*ጰራቅሊጦስ* የሚለው ቃል ከሦስቱ አካላት አንዱ ለኾነው ለእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ መጠሪያ ስሙ ሲኾን፣ ትርጕሙም በጽርዕ (ግሪክ) ቋንቋ ናዛዚ (የሚናዝዝ)፣ መጽንዒ (የሚያጸና)፣ መስተፍሥሒ (የሚያስደስት) ማለት ነው፡፡ በዓለ ጰራቅሊጦስ በሌላ ቃል በዓለ ጰንጠቆስጤ በመባልም ይታወቃል፡፡ ይኸውም በግሪክ ቋንቋ በዓለ ኀምሳ፣ የፋሲካ ኀምሳኛ ዕለት፣ በዓለ ሠዊት (የእሸት፣ የመከር በዓል) ማለት ነው /ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ ገጽ ፱፻፮ እና ፱፻፯/፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ካረገ በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ፲፪ቱ ደቀ መዛሙርት፣ ፸፪ቱ አርድእት፣ ፭፻ው ባልንጀሮችና ፴፮ቱ ቅዱሳት አንስት በኢሩሳሌም ከተማ በአንድነት ኾነው ለጸሎት ይተጉ ነበር፡፡ በሚያርግበት ጊዜም *እነሆ አባቴ የሰጠውን ተስፋ እኔ እልክላችኋለሁ፤ እናንተ ግን ከላይ ኃይል እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆዩ፤* /ሉቃ. ፳፬፥፵፱/ ሲል ለሐዋርያቱ በገባላቸው ቃል መሠረት ባረገ በ፲ኛው ቀን መንፈስ ቅዱስን ልኮላቸዋል፡፡

በሐዋርያት ሥራ እንደ ተጻፈው በበዓለ ጰራቅሊጦስ ማለዳ ኹሉም በአንድ ቦታ ተሰብስበው ሳሉ እንደ ዐውሎ ነፋስ ያለ ድምፅ ድንገት ከሰማይ መጣና የነበሩበትን ቤት ሞላው፡፡ ከዚያም እንደ እሳት የተከፋፈሉ የእሳት ላንቃዎች በኹሉም ላይ ተቀመጡባቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ኹላቸውም መንፈስ ቅዱስን ከተሞሉ በኋላ መንፈስ ቅዱስ ባደላቸው መጠን በየአገሩ ቋንቋዎች ኹሉ መናገር ጀመሩ /ሐዋ.፪፥፩-፬/፡፡ ጌታችን መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት የላከበት ይህ ዐቢይ በዓል ጰራቅሊጦስ ይባላል፡፡

ጌታችን ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ ከ፶ኛው፤ ከዐረገ ከ፲ኛው ቀን ጀምሮ እስከሚቀጥለው እሑድ ድረስ ያለው ወቅትም ዘመነ ጰራቅሊጦስ ተብሎ የሚጠራ ሲኾን፣ ይህ በዓል ካህናተ ኦሪት ዐሥራቱን፣ በኵራቱን፣ ቀዳምያቱን ይቀበሉበት ነበርና በብሉይ ኪዳን በዓለ ሠዊት ይባል ነበር፡፡ በበዓለ ጰራቅሊጦስም ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ተቀብለውበታልና በበዓለ ሠዊት ምትክ በዓለ ጰራቅሊጦስ ገብቶበታል፡፡

የበዓለ ትንሣኤ መነሻው የአይሁድ የፋሲካ በዓል ማለትም በግብፅ እስራኤል ከሞት የዳኑበት የመታሰቢያ በዓል እንደ ኾነው ኹሉ፣ ለበዓለ ጰራቅሊጦስም መነሻው ይኸው የአይሁድ የፋሲካ በዓል ነው፡፡ የአይሁድ ፋሲካ ከተከበረ ከሰባት ሳምንታት በኋላ በ፶ኛው ቀን የሩቆቹ ከከተሙበት ወጥተው፣ የቅርቦቹ ከተሰባሰቡበት ተገናኝተው ለበዓሉ ፍጻሜ የሚኾነውን በዓለ ሠዊት ያከብሩ ነበር፡፡

ከግብፅ እስከ ከነዓን ምድር የደረሰው የእንስሳት መሥዋዕት ሲጠናቀቅ በ፶ኛው ቀን ይሰባሰብ የነበረው የአይሁድ ጉባኤም መንፈስ ቅዱስ ከወረደበት ዕለት ጀምሮ ተበትኗል፡፡ መሥዋዕተ ኦሪቱ በአማናዊው መሥዋዕት በኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋና ደም እንደ ተለወጠ ኹሉ ጉባኤ አይሁድም በኢየሩሳሌም ከተማ በተሰበሰቡ በቅዱሳን ሐዋርያት ጉባኤ ተለውጧል (ተቀይሯል)፡፡ ይህችውም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ *ከኹሉ በላይ በምትኾን፣ ሐዋርያት በሰበሰቧት በአንዲት፣ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን፤* እንዳሉ ሠለስቱ ምእት /ጸሎተ ሃይማኖት/፡፡

ሐዋርያት በጽርሐ ጽዮን ተሰብስበው ሳሉ መንፈስ ቅዱስ በእሳት አምሳል ወርዶ ሰማያዊ ሀብትን፣ ዕውቀትና ጸጋን አድሏቸዋል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላም በአእምሮ ጎልምሰዋል፤ ጥቡዓን (ቈራጦች)፣ ጽኑዓን ኾነዋል፤ ለስብከተ ወንጌል የሚፋጠኑበትንና ለሰማዕትነት የሚዘጋጁበትን ልቡና ታድለዋል፡፡ ቀድሞ ይናገሩት ከነበሩት ከዕብራይስጥ ቋንቋ በተጨማሪ ፸፩ ቋንቋዎች ተገልጸውላቸው ምሥጢራትን መተርጐም ጀምረዋል፡፡ ሐዋርያት በየገአሩ ቋንቋ ሲናገሩ የሰሙ ከአይሁድ ወገን አንዳንዶቹም ሐዋርያትን *ጉሽ ጠጅ ጠጥተው ሰክረው የኾነ ያልኾነውን ይቀባጥራሉ* ይሏቸው ነበር፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም ይህንን ዐሳባቸውን በመንፈስ ቅዱስ አውቆ *ሰክረዋል የምትሉ እናንተ እንደምትጠራጠሩት አይደለም፡፡ ጊዜው ማለዳ፣ ሰዓቱም ገና ሦስት ሰዓት ነውና፡፡ ዳሩ ግን በነቢዩ ኢዩኤል ከዚህም በኋላ እንዲህ ይሆናል፤ መንፈሴን በሥጋ ለባሽ ሁሉ ላይ አፈስሳለሁ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችሁም ትንቢት ይናገራሉ፤ /ኢዩ.፪፥፳፰/ ተብሎ የተነገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ይህንን ድንቅ ተአምር ያደረገው እናንተ የሰቀላችሁት ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤* በማለት ሐዋርያት ኢየሱስ ክርስቶስ ነቢያት ትንቢት የተናገሩለት፣ ምሳሌ የመሰሉለት አምላክ ወልደ አምላክ መኾኑን፣ ከሙታን ተለይቶ መነሣቱን፣ ማረጉንና ዳግም በክብር በምስጋና መጥቶ በሕያዋንና በሙታን ላይ የሚፈረድ መኾኑን እንደሚመሰክሩ በአይሁድ ፊት አሰምቶ ተናገረ፡፡

በቅዱስ ጴጥሮስ ትምህርት የተማረኩ አሕዛብም *ምን እናድርግ* ብለው በጠየቁት ጊዜ ከክፋታቸው ተመልሰው፣ ንስሐ ገብተው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንዲጠመቁ ነገራቸው፡፡ በዚያችም ሰዓት ሦስት ሺህ ሕዝብ በኢየሱስ ክርስቶስ አምኖ ተጠምቋል /ሐዋ.፪፥፩-፵፩/፡፡ ይህም ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላ ያደረባቸው የማሳመን ጸጋና ተአምራትን የማድረግ ኃይላቸው እንደ በዛላቸው ያመላክታል፡፡

ይህ ዕለት ሀብተ መንፈስ ቅዱስ የተሰጠበት፤ ብዙ ሺሕ ምእመናን የተገኙበት ዕለት በመኾኑ ሊቃውንት የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን በማለት ይጠሩታል፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት *በዚህች ቀን በሦስት ሰዓት ኢየሱስ ክርስቶስ ጰራቅሊጦስን ልኮልናልና በላያችን ኃይልን ሞላ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ በሕያዋንና በሙታን ይፈርድ ዘንድ ሥልጣን እንዳለው በአዲስ ቋንቋ ተናገርን፤* በማለት በዕለቱ ያዩትንና የተደረገላቸውን፣ እንደዚሁም ስለ በዓሉ ታላቅነት ከመሰከሩ በኋላ ይህንን በዓል ማክበር እንደሚገባ አዝዘዋል፤ በአንጻሩ በዚህ ወቅት (በበዓለ ኀምሳ) መጾምና ማዘን ተገቢ አለመኾኑን ተናግረዋል /ዲድስቅልያ ፴፥፴፰-፴፱፤ ፴፩፥፷፱-፸/፡፡

የጰራቅሊጦስ መዝሙርና ምንባባት

በዓለ ጰራቅሊጦስ ከዘጠኙ የጌታችን ዐበይት በዓላት አንዱ ሲኾን በዕለቱ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው የቅዱስ ያሬድ መዝሙርም ይትፌሣሕ የሚለው የትንሣኤ መዝሙር ነው፡፡ እንደ መዝሙሩ ኹሉ በጰራቅሊጦስ በዓል በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የቅዱሳት መጻሕፍት ክፍሎችም በትንሣኤ ዕለት የተነበቡት ምንባባት ናቸው፡፡

እነዚህም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ በመነሣቱ፣ በማረጉና መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት በመላኩ፤ እንደዚሁም ሥጋውን ቈርሶ፣ ደሙን አፍስሶ የሰውን ልጅ ከዘለዓለም ሞት በማዳኑ የሰው ዘር ብቻ ሳይኾን የሰማይ መላእክት፣ የምድር ፍጥረታት ሳይቀሩ ሐሤት እንደሚያደርጉ፤ ምድርም በክርስቶስ ደም በመንጻቷ የጌታችንን ትንሣኤ በደስታ እንደምታከብር ያስረዳሉ፡፡

ከበዓለ ጰራቅሊጦስ በኋላ ባሉት ሰንበታት (እሑዶች) የሚዘመሩ መዝሙራት ትንሣኤን፣ ዕርገትን፣ የመንፈስ ቅዱስን መውረድ የሚያስረዱ ሲኾኑ፣ ዓላማቸውም ከሙታን ተለይቶ ለተነሣው፣ አዳምና ልጆቹን ከዲያብሎስ ባርነትና ከሲኦል ላወጣቸው ለልዑል እግዚአብሔር ምስጋና ማቅረብ ነው፡፡

ከዚሁ ኹሉ ጋር ለማሳሰብ የምንፈልገው ቁም ነገር በዓለ ጰራቅሊጦስን ተከትለው ሁለት ዐበይት አጽዋማት ይጀመራሉ፡፡ እነዚህም ጾመ ሐዋርያት እና ጾመ ድኅነት (ረቡዕና ዓርብ) ሲኾኑ፣ ቍጥራቸውም ከሰባቱ አጽዋማት ውስጥ ነው፡፡ ስለኾነም ኹላችንም ልንጾማቸው እንደሚገባ በቤተ ክርስቲያን ሕግ ታዝዟል፡፡ ይህም ከቀደሙ አባቶቻችን ጀምሮ የመጣ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሥርዓት እንጂ እንግዳ ሕግ አይደለም፡፡

ቅዱሳት መጻሕፍት እንደሚናገሩት በብሉይ ኪዳን ነቢዩ ሙሴ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቀበለውን ሕገ ኦሪት ለሕዝቡ ከማስተማሩ በፊት ጾሟል /ዘፀ.፴፬፥፳፰/፡፡ ቅዱሳን ነቢያትም የተስፋውን ቃል መፈጸም እየተጠባበቁ እግዚአብሔርን ውረድ፤ ተወለድ እያሉ ይጾሙ፣ ይጸልዩ ነበር፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ጾም የምግባር መሠረት መኾኑን ሊያስተምረን ወንጌልን ከመስበኩ አስቀድሞ ጾሟል /ማቴ.፬፥፩-፲፩/፤ ሐዋርያትም በበዓለ ኀምሳ መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላ ሕገ ወንጌልን ለሕዝቡ ከማስተማራቸው አስቀድሞ ጾመዋል፡፡

እኛም እነርሱን ተከትለን፣ በእነርሱ ሥርዓት በመመራት፣ በሐዋርያት ላይ ያደረው የመንፈስ ቅዱስ ጸጋና ሀብት በእኛም ላይ እንዲያድርብን በየዓመቱ ጾመ ሐዋርያትንና ሌሎችንም አጽዋማት መጾም እንደሚገባን በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ተወስኗል /ፍት.ነገ. ፲፭፥፭፹፮/፡፡

ጾመ ድኅነት ስሙ እንደሚያመለክተው የመዳን ጾም ማለት ሲኾን፣ ይህም በብሉይ ኪዳኑ አጽዋማት በጾመ አስቴር እና በጾመ ዮዲት የተተካ የሐዲስ ኪዳን ጾም ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን በሐማ ምክንያት በእስራኤል ላይ ታውጆ የነበረው ሞት በጾመ አስቴር እንደ ተሻረ ኹሉ፣ በሐዲስ ኪዳንም በዕለተ ረቡዕ በጌታችን ላይ በተፈጸመው ምክር የሰይጣን ሴራ ፈርሷልና በጾመ አስቴር ምትክ ረቡዕን እንጾማለን፡፡

እንደዚሁም በብሉይ ኪዳን በጾመ ዮዲት ምክንያት ሆሎሆርኒስ ድል እንደ ተደረገበት ኹሉ፣ በሐዲስ ኪዳንም መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዓርብ በመስቀል ላይ በከፈለው መሥዋዕትነት ዲያብሎስ ድል ተደርጓልና በጾመ ዮዲት ምትክ ዓርብን እንጾማለን፡፡ የእነዚህ የሁለቱ ቀናት (የረቡዕና ዓርብ) ጾም ጾመ ድኅነት ይባላል፡፡

በአጠቃላይ ጾመ ሐዋርያትና ጾመ ድኅነት እንደ ጾመ ነነዌና ዐቢይ ጾም የበዓላትና የአጽዋማት ማውጫ ቀመርን ተከትለው የሚመጡ ከሰባቱ አጽዋማት መካከል የሚመደቡ ጾሞች ናቸው፡፡ የጾመ ሐዋርያት ፋሲካ (መፈጸሚያ) የቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ በዓለ ዕረፍት (ሐምሌ ፭ ቀን) ሲኾን፣ ጾመ ድኅነት ግን ከበዓለ ኀምሳ በስተቀር ዓመቱን ሙሉ የሚጾም ጾም ነው፡፡

ዕለተ ረቡዕ የጌታ ሞት የተመከረበት፤ ዓርብም አምላካችን የተሰቀለበት ዕለት ነውና በመስቀሉ መሥዋዕትነት ያገኘውን ድኅነት ዘወትር ማሰብ ስለሚገባን ሁልጊዜ እንድንጾማቸው በቅዱስ ሲኖዶስ ሥርዓት ተሠርቶልናል፡፡ በዚህ ዓመት ጾመ ሐዋርያት ሰኔ ፲፫፤ ጾመ ድኅነት ደግሞ ሰኔ ፲፭ ቀን ይጀመራሉ፡፡ በመኾኑም እንደ ክርስቲያን የምንጠቀመው በራሳችን መልካም ተግባር፤ የምንወቀሰውም በራሳችን መጥፎ ድርጊት መኾኑን ተረድተን ይኼ የቄሶች፤ ይኼ የመነኰሳት ነው የሚል ሰበብ ሳንፈጥር ኹላችንም በአንድነት ብንጾማቸው ከእግዚአብሔር ዘንድ የምናገኘው ጸጋና ሀብት ይበዛልናልና ራሳችንን ለጾም እናዘጋጅ፡፡

በዓለ ትንሣኤውን በደስታ እንድናሳልፍ ፈቅዶ እስከ ዛሬ ድረስ እንዳቆየን፣ አሁን ደግሞ በጾም፣ በጸሎት ኾነን እርሱን የምናመሰግንበትን ወቅት ስላመጣልን አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ስሙ ለዘለዓለሙ የተመሰገነ ይኹን፡፡

ምንጭ፡-

መጽሐፈ ስንክሳር፣ ግንቦት ፲፰ ቀን፡፡

መጽሐፈ ግጻዌ ዘደብር ዓባይ፣ ሊቀ ሥልጣናት አባ ጥዑመ ልሳን፤ አዲስ አበባ፣ ፳፻፩ ዓ.ም፡፡

መዝገበ ታሪክ፣ ክፍል ፪፣ ገጽ ፹፬-፹፭፣ መ/ር ኅሩይ ኤርምያስ፣ ፲፱፻፺፭ ዓ.ም፡፡

ማኅቶተ ዘመን ገጽ ፻፺፭-፪፻፬፣ መ/ር በሙሉ አስፋው፤ ፳፻፩ ዓ.ም፡፡

ዘመነ ዕርገት

ሰኔ ፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ዕርገት በግእዝ ቋንቋ ማረግ፣ ከታች ወደ ላይ መውጣት ማለት ሲኾን የጌታችን ትንሣኤ በተከበረ በዐርባኛው ቀን የሚውለው ዐቢይ በዓልም ዕርገት ይባላል /ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ ገጽ ፯፻፷/፡፡

እንደምናስታውሰው ባለፈው ሐሙስ (ሰኔ ፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም) ከጌታችን ከመድኀኒታችን ኢየሱስ ዐበይት በዓላት መካከል አንዱ የኾነው በዓለ ዕርገት በቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ተከብሯል፡፡ ከጌታችን የዕርገት በዓል ጀምሮ (ከዐርባኛው ቀን) እስከ ጰራቅሊጦስ ዋዜማ (ዐርባ ዘጠነኛው ቀን) ድረስ ያለው ወቅት ዘመነ ዕርገት ይባላል፡፡

በዓለ ዕርገት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ከተነሣ በኋላ ለዐርባ ቀናት በግልጽም በስውርም ለቅዱሳን ሐዋርያትና ለቅዱሳት አንስት መጽሐፈ ኪዳንን፣ ትርጓሜ መጻሕፍትን፣ ምሥጢራትን፣ ሕግጋትንና ቀኖናተ ቤተ ክርስቲያንን ሲያስተምር ቆይቶ ወደ ቀደመ ዙፋኑ ወደ ሰማይ ማረጉን የምንዘክርበት ታላቅ የደስታ ቀን ነው፡፡

መጽሐፈ ስንክሳር በዓለ ዕርገት የክብር ባለቤት ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእኛ በነሣው ሥጋ ከአባቱና ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ ወዳለው የአንድነት አኗኗሩ ወደ ሰማይ ያረገበት ዕለት መኾኑን ጠቅሶ፣ በዚህች ቀን ያን ጊዜ በኪሩቤል ላይ ተቀምጦ ወጣ፤ በነፋሳትም ክንፎች ላይ ኹኖ ወጣ /መዝ.፲፯፥፲/ የሚለው የዳዊት ትንቢት መፈጸሙን ያትታል፡፡

በተጨማሪም ሌሊት በራእይ አየሁ፤ እነሆም እንደ ሰው ልጅ የሚመስል በሰማይ ደመና መጣ፤ በዘመናትም ወደ ሸመገለው ደረሰ፡፡ ወደ ፊቱም አቀረቡት፡፡ ወገኖችና አሕዛብ፣ በልዩ ልዩ ቋንቋም የሚናገሩ ኹሉ ይገዙለት ዘንድ ግዛትና ክብር፣ መንግሥትም ተሰጠው፡፡ ግዛቱም የማያልፍ የዘለዓለም ግዛት፤ መንግሥቱም የማይጠፋ ነው፤ /ዳን.፯፥፲፫-፲፬/ የሚለው የነቢዩ ዳንኤል ትንቢት በጌታችን ዕርገት መፈጸሙን ይናገራል /ስንክሳር፣ ግንቦት ፰ ቀን/፡፡

ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም ዐርባ ስድስተኛውን መዝሙረ ዳዊት በተረጐመበት አንቀጹ ድል መንሳት ባለበት የነጋሪት ድምፅ እግዚአብሔር ዐረገ አለ እንጂ መላእክት አሳረጉት አላለም፡፡ በፊቱ መንገድ የሚመራው አልፈለገም፡፡ በዚያው ጎዳና እርሱ ዐረገ እንጂ፤ በማለት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአምላካዊ ሥልጣኑ ወደ ሰማይ ማረጉን ተናግሯል፡፡

በተመሳሳይ ምሥጢርም የጌታችንን ዕርገት ከነቢዩ ኤልያስ ዕርገት ጋር በማነጻጸር ነቢዩ ኤልያስ በመላእክት ርዳታ ወደ ሰማይ መወሰዱን /፪ኛነገ.፪፥፩-፲፫/፤ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን የመላእክት ፈጣሪ ነውና በእነርሱ ርዳታ ሳይኾን በገዛ ሥልጣኑ ማረጉን ያስረዳል /ሐዋ.፩፥፱-፲፪/፡፡

ሊቁ በተጨማሪም ሕማም የሚስማማው ግዙፍ ሥጋን ተዋሕዶ ሳለ ከስቅለቱ አስቀድሞ በባሕር ላይ ከሔደ፣ ዛሬ ነፋስን ከፍሎ ሲያርግ ቢታይ ማንም ማን አይጠራጠር፡፡ ሥጋው አልተለወጠምና፤ በማለት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሞቱና ከትንሣኤው አስቀድሞ በውኀ ላይ እንደተራመደ ኹሉ፣ በለበሰው ሥጋ ወደ ሰማይ ማረግም እንደሚቻለው አስረድቷል /ሃይማኖተ አበው ዘዮሐንስ አፈወርቅ፣ ከፍል ፲፫፣ ምዕ.፷፯፥፲፪-፲፭/፡፡

በበዓለ ዕርገት ሊቃውንቱ ሌሊት በማኅሌት፣ በዝማሬ እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ ያድራሉ፡፡ ሥርዓተ ማኅሌቱ እንዳበቃ የሚሰበከው የነግህ ምስባክም፡- ዘምሩ ለእግዚአብሔር ዘዐርገ ውስተ ሰማይ ሰማይ ዘመንገለ ጽባሕ ናሁ ይሁብ ቃሎ ቃለ ኃይል /መዝ.፷፯፥፴፫/ የሚለው የዳዊት መዝሙር ሲኾን ቀጥተኛ ትርጕሙም በምሥራቅ በኩል ወደ ሰማየ ሰማያት ለወጣ (ላረገ) ለእግዚአብሔር ዘምሩ፤ የኀይል የኾነውን ቃሉን እነሆ ይሰጣል የሚል ኾኖ ምሥጢሩም ነፍሳትን ይዞ ከሲኦል ወደ ገነት ለወጣ፤ አንድም በደብረ ዘይት በኩል ላረገ ለእግዚአብሔር ምስጋና አቅርቡ ማለት ነው፡፡

በተመሳሳይ መልኩ ጌታችን ባረገ በዐሥረኛው ቀን የኀይል ቃል የተባለ መንፈስ ቅዱስን ለሐዋርያት መላኩን፤ እንደዚሁም ይህ ከእናንተ ወደ ሰማይ የወጣው ኢየሱስ ወደ ሰማይ ሲሔድ እንዳያችሁት፣ እንዲሁ ይመጣል፤ ተብሎ እንደ ተጻፈ /ሐዋ.፩፥፲፩/፣ ጌታችን ዳግም እንደሚመጣ፤ እኛም ይህንን የጌታችንን የማዳን ሥራ እያደነቅን ለእርሱ ምስጋና፣ ዝማሬ ማቅረብ እንደሚገባን ያስረዳል፡፡

የነግህ ወንጌል (ከቅዳሴ በፊት የሚነበበው) ደግሞ የሉቃስ ወንጌል ምዕራፍ ፳፬ ቍጥር ፵፭ እስከ መጨረሻው ድረስ ያለው ኃይለ ቃል ሲኾን፣ ኃይለ ቃሉም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማየ ሰማያት እንደሚወርድ፣ የሰውን ልጅ ለማዳን ሲል መከራ እንደሚቀበል፣ እንደሚሞት፣ ከሙታን ተለይቶ እንደሚነሣ፣ ወደ ሰማይ እንደሚያርግና ዳግም እንደሚመጣ በነቢያት የተነገረው ትንቢት መፈጸሙንና ለዚህም ቅዱሳን ሐዋርያት ምስክሮች መኾናቸውን ማለትም በመላው ዓለም እየዞሩ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ የማዳን ሥራ እንደሚሰብኩና በሰማዕትነት እንደሚያልፉ፤ እንደዚሁም ሰማያዊ ሀብትንና ዕውቀትን እስኪያገኙ ድረስ በኢየሩሳሌም እንዲቆዩ መታዘዛቸውን ያስረዳል /ትርጓሜ ወንጌል/፡፡

ይህ ምሥጢር ለጊዜው ሐዋርያትን የሚመለከት ይኹን እንጂ ፍጻሜው ግን ኹላችንም ቅዱሳት መጻሕፍት የተናገሩትን ቃል አብነት አድርገን የእግዚአብሔርን ሰው መኾንና የማዳኑን ሥራ አምነን፣ ሌሎችንም በማሳመን በሃይማኖታችን ጸንተን መኖር እንደሚገባን፤ እግዚአብሔር አምላካችን ኃይሉን፣ ጸጋውን፣ ረድኤቱን እንዲያሳድርብንም ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን መለየት እንደሌለብን የሚያስገነዝብ መልእክት አለው፡፡

በዕለተ ዕርገት በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችም ከቅዱስ ጳውሎስ መልእክት ዕብራውያን ፩፥፩ እስከ ፍጻሜው ድረስ፤ ከሌሎች መልእክታት ደግሞ ፩ኛ ጴጥሮስ ፫፥፲፰-ፍጻሜየሐዋርያት ሥራ ፩፥፩-፲፪ ሲኾኑ፣ ምስባኩም ዐርገ እግዚአብሔር በይባቤ ወእግዚእነ በቃለ ቀርን ዘምሩ ለአምላክነ ዘምሩ የሚለው ኾኖ /መዝ.፵፮፥፭-፮/፣ መልእክቱም በዕልልታና በመለከት ድምፅ ላረገ ለአምላካችን፣ ለጌታችንና ለመድኀኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ምስጋና አቅርቡ ማለት ነው፡፡

ወንጌሉ ደግሞ፣ ማርቆስ ፲፮፥፲፬ እስከ ፍጻሜ ድረስ ሲኾን ቃሉም በነግህ ከተነበበው የወንጌል ክፍል ቃል ተመሳሳይነት አለው፡፡ ቅዳሴውም ቅዳሴ ዲዮስቆሮስ ሲኾን ይኸውም ከሦስቱ አካላት አንዱ የኾነውን የእግዚአብሔር ወልድን (የኢየሱስ ክርስቶስን) ዘለዓለማዊነት የሚያስረዳ፤ ሥጋዌዉን፣ ሕማሙን፣ ሞቱን፣ ትንሣኤዉን፣ ዕርገቱንና ዳግም ምጽአቱንም የሚናገር በመኾኑ በዘመነ ትንሣኤ፣ በዘመነ ዕርገትና በበዓለ ሃምሳ ይቀደሳል፡፡

ቅዱስ ዲዮስቆሮስ በቅዳሴዉ መጀመሪያ ላይ ሀልዎተ እግዚአብሔርንና ምሥጢረ ሥላሴን መሠረት በማድረግ ለእግዚአብሔር ምስጋና ካቀረበ በኋላ፣ ቍጥር ፴፩ ላይ ደግሞ ወበ፵ ዕለት አመ የዐርግ ሰማየ አዘዞሙ እንዘ ይብል ጽንሑ ተስፋሁ ለአብ፤ ከሙታን ተለይቶ በተነሣ በዐርባኛው ቀን በብርሃን፣ በሥልጣን፣ በይባቤ ወደ ሰማይ በሚያርግበት ጊዜ አብ የሚሰድላችሁ መንፈስ ቅዱስን እስክትቀበሉ ድረስ ከዚህ ቆዩ ብሎ አዘዛቸው፤ በማለት መጽሐፍ ቅዱሳዊ በኾነ ቋንቋ የጌታችንን ወደ ሰማይ ማረግና ለሐዋርያት የሰጠውን አምላካዊ ትእዛዝ ይናገራል /ሉቃ.፳፬፥፵፱/፡፡

በዘመነ ዕርገት ውስጥ በሚገኘው እሑድ (ሰንበት) ሌሊት ሊቃውንቱ የሚያደርሱት መዝሙርም በሰንበት ዐርገ ሐመረ የሚል ሲኾን ይኸውም ጌታችን በሰንበት ወደ ታንኳ በመውጣት ባሕርንና ነፋሳትን እንደ ገሠፀ፤ ሐዋርያቱንም ጥርጥር ወደ ልቡናችሁ አይግባ፤ አትጠራጠሩ እንዳላቸው፤ እንደዚሁም ወንጌልን ይሰብኩ፣ ያስተምሩ ዘንድ በመላው ዓለም እንደሚልካቸው፤ በሰማያዊ መንግሥቱ ይኖሩ ዘንድም ዳግመኛ መጥቶ እንደሚወስዳቸው የሚያስገነዝብ መልእክት አለው /ሉቃ.፰፥፳፪-፳፬፤ ዮሐ.፲፬፥፪፤ ፳፥፳፩/፡፡

በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ ምንባባትም በዕለተ ዕርገት (ሐሙስ) ከተነበቡት ጋር ተቀራራቢነት ያላቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ናቸው፡፡ ለማስታወስ ያህልም ከጳውሎስ መልእክት ሮሜ ፲፥፩ እስከ ፍጻሜው፤ ከሌሎች መልእክታት ፩ኛ ጴጥሮስ ፫፥፲፭ እስከ ፍጻሜው ድረስ ይነበባሉ፡፡ የሐዋርያት ሥራ፣ ምስባኩና ቅዳሴው ከሐሙስ ዕለቱ (ከዕርገት) ጋር አንድ ዓይነት ሲኾን ወንጌሉም ሐሙስ ጠዋት (በነግህ) የተነበበው ሉቃ.፳፥፵፭ እስከ ፍጻሜው ድረስ ያለው ኃይለ ቃል ነው፡፡

በዘመነ ዕርገት ከቅዳሴ በኋላ ከሚቀርቡ ዝማሬያት መካከል ዐርገ ሰማያተ በዐምደ ደመና የሚለው አንደኛው ሲኾን፣ ይህ ዝማሬ ከድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ፣ ከነፍሷ ነፍስ የነሣ (የተዋሐደ)፤ ለእስራኤላውያን በሲና በረኀ መና ያወረደ፤ ሶስናን ከረበናት እጅ ያዳነ፤ ሰንበትን ለሰው ልጆች ዕረፍት የሠራ፤ የክርስትና ሃይማኖትን ያቀና (የመሠረተ)፤ ከሰማይ የወረደው የሕይወት እንጀራ፤ በባሕርዩ ምስጋና የሚገባው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደመና ተጭኖ ወደ ሰማይ ማረጉን የሚያስረዳ ሰፊ ምሥጢር አለው፡፡

በአጠቃላይ በዘመነ ዕርገት በማኅሌት፣ በቅዳሴ፣ በመሥዋዕት ጊዜ በቤተ ክርስቲያን የሚሰጡ ትምህርታት፣ የሚቀርቡ መዝሙራትና የሚነበቡ መጻሕፍት የእግዚአብሔርን ሰው መኾን፣ ተአምራቱን፣ ሕማሙን፣ ሞቱን፣ ነፍሳትን ከሲኦል ማውጣቱን፣ ትንሣኤውን፣ ለሐዋርያትና ለቅዱሳት አንስት መግለጡን፣ በተለይ ደግሞ ዕርገቱን፣ ዳግም ምጽአቱንና ምእመናን በእርሱ አምነው የሚያገኙትን ድኅነት፣ ጸጋና በረከት፣ እንደዚሁም ስለ መንግሥተ ሰማያት የሚያስረዳ ይዘት አላቸው፡፡

ከዚህ በተጨማሪ ምርኮን (የነፍሳትን ወደ ገነት መማረክ) የሚያትቱ ትምህርቶች የሚሰጡትም በዚህ በዘመነ ዕርገት ወቅት ሲኾን፣ ይኸውም በሰይጣን ባርነት ተይዘው የኖሩ ነፍሳት ነጻ የወጡት በኢየሱስ ክርስቶስ አምላካዊ ሥልጣን በመኾኑ ነው፡፡ ምርኮን ማረከህ፤ ወደ ሰማይም ወጣህ፡፡ ስጦታህንም ለሰዎች ሰጠህ፡፡ ያድሩ ዘንድ ይክዱ ነበርና እንዳለ ቅዱስ ዳዊት /መዝ.፷፯፥፲፰/፡፡ ይህም ጌታችን ነፍሳትን ይዞ ከሲኦል ወደ ገነት መውጣቱንና ለምእመናን የሥላሴ ልጅነትን እንደሰጠ የሚያስረዳ ሲኾን፣ ያድሩ ዘንድ ይክዱ ነበር ሲልም በክህደት ይኖሩ የነበሩ ኹሉ ጌታችን በሰጠው ልጅነት ተጠርተው፣ አምነውና በሃይማኖት ጸንተው መኖራቸውን ሲያመለክት ነው፡፡

ከላይ እንደ ተመለከትነው ዘመነ ዕርገት ወደ ላይ የመውጣት፣ የማረግ፣ ከፍ ከፍ የማለትና የማደግ ወቅት ነው፡፡ እኛም በሞት ከመወሰዳችን በፊት ለመንግሥቱ የሚያበቃ ሥራ ያስፈልገናልና ሕሊናችን በጽድቅ ሥራ እንዲያርግ (ከፍ ከፍ እንዲል) ዘወትር በጾም፣ በጸሎት መትጋት ይኖርብናል፡፡ ምክንያቱም ዕርገት ሲባል በአካል ማረግን ወይም ወደ ሰማይ መውጣትን ብቻ ሳይኾን፣ በአስተሳሰብና በምግባር መለወጥን፣ በአእምሮ መጎልመስንም ያመለክታልና፡፡

በሞቱ ሕይወታችንን ለመለሰልን፤ በትንሣኤው ትንሣኤያችንን፣ በዕርገቱ ክብራችንን ለገለጠልን ለጌታችን ለመድኀኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ለዘለዓለሙ ክብር ምስጋና ይደረሰው፡፡ ዜና ብሥራቱን፣ ፅንሰቱን፣ ልደቱን፣ ዕድገቱን፣ ስደቱን፣ ተአምራቱን፣ ሕማሙን፣ ሞቱንና ትንሣኤውን በሰማንበት ዕዝነ ልቡናችን፣ ባየንበት ዓይነ ሕሊናችን ዕርገቱንም እንድንሰማና እንድናይ ዕድሜ ለንስሐ ሰጥቶ እስከ ዛሬ ድረስ እንደ ጠበቀን ኹሉ፣ ዳግም ለፍርድ በሚመጣበት ጊዜም እናንተ ቡሩካን ወደ እኔ ኑ የሚለውን የሕይወት ቃል እንዲያሰማን ቅዱስ ፈቃዱ ይኹንልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡-

መጽሐፍ ቅዱስ፣ የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር፤ አዲስ አበባ፣ ፳፻ ዓ.ም፡፡

መዝሙረ ዳዊት ንባቡና ትርጓሜው፣ ተስፋ ገብረ ሥላሴ፤ አዲስ አበባ፣ ፲፱፻፹፪ ዓ.ም፡፡

ማኅቶተ ዘመን፣ መ/ር በሙሉ አስፋው፣ ገጽ ፻፺፩-፻፺፬፤ አዲስ አበባ፣ ፳፻፩ ዓ.ም፡፡

ዝማሬ ወመዋሥዕት፣ ትንሣኤ ማሳተሚያ ድርጅት፤ አዲስ አበባ፣ ፲፱፻፹፱ ዓ.ም፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማእከል

ግንቦት ፳፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅድስት፣ አሐቲ፣ ከኹሉ በላይ የኾነች፣ በክርስቶስ ደም የተመሠረተች፣ በቅዱሳን ነቢያት ትንቢት የጸናች፣ በቅዱሳን ሐዋርያት ስብከት የታነፀች፣ በሊቃውንት አስተምህሮ የጸናች፣ በምእመናን ኅብረት የተዋበች ንጽሕት ማኅደረ ሃይማኖት ናት፡፡

የዚህችን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ምእመናን ይረዱ ዘንድ ልዩ ልዩ ዘዴዎችን መጠቀም ይገባል፡፡ ከእነዚህ ዘዴዎች አንዱ ከሰሞኑ በማኅበረ ቅዱሳን አማካይነት በአዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ለዕይታ ቀርቦ የሰነበተው ዓይነት ዐውደ ርእይ አንዱ ነው፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን አምስተኛውን ዐውደ ርእይ ለምእመናን ሊያቀርብ የነበረው ከመጋቢት ፲፭-፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የነበረ ቢኾንም ዳሩ ግን ዐውደ ርእዩ በሰዓቱ ግልጽ ባልነበረ ምክንያት ላልተወሰነ ጊዜ ታግዶ ከቆየ በኋላ እግዚአብሔር ሥራውን የሚሠራበት ጊዜ ሲደርስ እነሆ ከግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ጀምሮ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ለተመልካቾቹ ይፋ ኾነ፡፡

በዚህ ዐውደ ርእይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት፣ ዶግማ፣ ቀኖና እና ትውፊት በሰፊው ቀርቦ በምእመናን ሲታይ ሰንብቷል፡፡ በተጨማሪም በአንድነት ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገልና የተቸገሩትን ለመርዳት የጎላ ድርሻ ያላቸው የጽዋ፣ የበጎ አድራጎትና የጉዞ ማኅበራት አገልግሎትም ተዳስሷል፡፡

ሊቃውንቱና ደቀ መዛምርቱ በዐውደ ርእዩ የሚሳተፉትን ጎብኝዎች ለማስደሰት የአገር ርቀት ሳይገድባቸው፣ መንገድ ሳያደክማቸው ከየመኖሪያ ቦታቸው በመምጣት በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ለሳምንት ያህል ቆይተዋል፡፡

ዐውደ ርእዩ በአራት ዐበይት አርእስት ማለትም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት፣ የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልዕኮ፣ የቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ እና ምን እናድርግ በሚሉ የተከፋፈለ ሲኾን በእያንዳንዱ ትዕይንት ሥርም በርካታ አርእስት ተካተውበታል፡፡ እያንዳንዳቸው የያዟቸው ጭብጦችም የሚከተሉት ናቸው፤

ትዕይንት አንድ፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት

ይህ ትዕይንት ሀልዎተ እግዚአብሔር፣ ነገረ ድኅነት፣ ነገረ ማርያም፣ ነገረ ቅዱሳን እና ነገረ ቤተ ክርስቲያን የሚዳሰሱበት ክፍል ሲኾን፣ በውስጡም ሀልዎተ እግዚአብሔር፣ እግዚአብሔር አምላክ በጊዜና በቦታ የማይወሰን፣ መጀመሪያና መጨረሻ የሌለው፣ የፍጥረታት ኹሉ አስገኚና እርሱ በገለጠው መጠን ብቻ የሚታወቅ እንጂ ባሕርዩ ተመርምሮ ሊደረስበት እንደማይቻል እንደዚሁም መልዕልተ ኵሉ (የኹሉ የበላይ) መኾኑን ያስረዳል፡፡

እግዚአብሔር ሲባልም አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ማለት እንደኾነ፤ እንደዚሁም እግዚአብሔር አምላክ በሥነ ፍጥረቱ፣ በአምላካዊ መግቦቱ፣ በሕሊና፣ በቅዱሳት መጻሕፍት፣ በዓለም ላይ በሚፈጸሙ ድርጊቶች ምስክርነት፣ ሥጋን በመልበስራሱን ለእኛ እንደገለጠልን በዚህ ትዕይንት ተብራርቷል፡፡

በተጨማሪም ሃይማኖት ማለት እግዚአብሔር ራሱን ለሰው ልጅ የገለጠበት መንገድ ስለመኾኑና ስለ አብርሃም እግዚአብሔርን ፈልጎ ማግኘት፣ በተጨማሪም በዓለም ላይ ብዙ ሃይማኖቶች ለመኖራቸው ምክንያቱ የሰይጣን ክፉ ሥራና የሰው ልጅ የመረዳት ዓቅም መለያየት ስለመኾኑ ተብራርቶበታል፡፡

ነገረ ድኅነት ደግሞ በአዳምና በሔዋን ምክንያት የዘለዓለም ሞት ተፈርዶበት የነበረው የሰው ልጅ ከሦስቱ አካላት አንዱ በኾነው በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሕማማተ መስቀልና ሞት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ መቻሉን በማስረዳት እመቤታችን የመልአኩን ብሥራት ከሰማችበት ጊዜ ጀምሮ የጌታችን ፅንሰት፣ ልደት፣ስደት፣ ዕድገት፣ ጥምቀት፣ ትምህርት፣ ተአምራት፣ ሕማማት፣ ሞት፣ ትንሣኤ፣ ዕርገትና ዳግም ምጽአት የነገረ ድኅነት መሠረቶች መኾናቸውን ይተነትናል፡፡

እንደዚሁም እምነት፣ ምግባር እና ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንን መፈጸም የሰው ልጆች ለመዳን ሊያሟሏቸው የሚገቡ ቅድመ ኹኔታዎች መኾናቸው በዚህ ርእስ ሥር ተካቷል፡፡

ነገረ ማርያምም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የአምላክ እናት እንደመኾኗ ከመፅነሷ በፊት፣ በፅንሷ ጊዜም ኾነ ከፀነሰች በኋላ ዘለዓለም ድንግል ስለመኾኗ እንደዚሁም በእግዚአብሔር ፊት ቆማ ለእኛ እንደምታማልድ ያስረዳል፡፡

ነገረ ቅዱሳን ደግሞ ሰማያውያን መላእክትን ጨምሮ ያላቸውን ኹሉ ትተውእግዚአብሔርን ብቻ የተከተሉ፣ መከራ መስቀሉን ተሸክመው ሕይዎታቸውን በሙሉበ ተጋድሎ ያሳለፉ፣ በፍጹም ልቡናቸው ጸንተው እስከ መጨረሻው ድረስ እግዚአብሔርን የተከተሉቅዱሳን አባቶች እና እናቶች ከእግዚአብሔር በተሰጣቸው ጸጋና ሥልጣን በምድርም በሰማይም እንደሚያማልዱ ያስረዳል፡፡

በነገረ ቤተ ክርስቲያን ሥር ደግሞ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስአካል፣ የምእመናን ኅብረት፣ የሰው ልጆችና የመላእክት፣ በዓለመ ሥጋና በዓለመ ነፍስ ያሉ እንደዚሁም የሥውራንም የገሃዳውያንም (በግልጽ የሚታዩ)ምእመናን አንድነትመኾኗ፣ ይህቺ ቤተ ክርስቲያን በተጋድሎ ብትኖርም ነገር ግን ድል አድራጊ፤ በባሕርዩአም ቅድስት፣ አሐቲ (አንዲት)፣ ሐዋርያዊት፣ ኵላዊት እንደኾነች ተተንትኖበታል፡፡

ትዕይንት ሁለት፡- የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልእኮ

በዚህ ትዕይንት የሐዋርያነትና የሐዋርያዊ አገልግሎት ትርጕም፣ ዓላማና አመሠራረትን ጨምሮ ስብከተ ወንጌል አንዴት እንደ ተስፋፋና እስከ ዛሬ ድረስ በቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሱ ፈተናዎችና መልካም አጋጣሚዎች የተካተቱበት ልዩ ልዩ መረጃና ትምህርት ቀርቦበታል፡፡

የሐዋርያዊ አገልግሎት መጀመርና መስፋፋት በኢትዮጵያ በሚለው የዚህ ትዕይንት ንዑስ ርእስ ሥር ከ፩ኛው እስከ ፯ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ የነበረው ሐዋርያዊ አገልግሎት ተዳሶበታል፡፡ የአባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን፣ የቅዱሳን ነገሥታት አብርሀ እና አጽብሀ፣ የዘጠኙ ቅዱሳን፣ የዐፄ ካሌብና የቅዱስ ያሬድ ሐዋርያዊ አገልግሎት ለስብከተ ወንጌል መስፋፋት ያደረገው አስተዋፅዖ በርእሱ የተገለጡ የታሪክ ክፍሎች ናቸው፡፡

ሁለተኛው ንዑስ ርእስ ደግሞ ከ፰ኛው እስከ ፲ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ በዮዲት ጉዲት ምክንያት ቅዱሳት መጻሕፍትና አብያተ ክርስቲያናት በመቃጠላቸው፣ ሊቃውንቱና ምእመናኑ በመገደላቸውና በመሰደዳቸው በቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት ላይ ጉዳት እንደ ደረሰ ያስረዳል፡፡

በሦስተኛ ደረጃ በዮዲት ጉዲት ዘመን በደረሰው በደል ቁጭት ያደረባቸው አባቶች በመነሣታቸው ምክንያት ከዐሥራ ፲፩ኛው እስከ ፲፮ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበረውን የሐዋርያዊ ተልዕኮ ትንሣኤ በመግለጽ ለዚህም የአራቱ ቅዱሳን ነገሥታት (ይምርሃነ ክርስቶስ፣ ሐርቤ/ገብረ ማርያም፣ ላሊበላና ነአኵቶ ለአብ) መነሣት፤ የሐይቅ እስጢፋኖስ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ገዳም መመሥረትና እንደ አቡነ ተክል ሃይማኖት ያሉ አባቶች፣ እንደዚሁም በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብና በዘመኑ የነበሩ አበው የስብከተ ወንጌል አገልግሎት፤ በተጨማሪም እንደ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ያሉ ቅዱሳን መጻሕፍትን በማዘጋጀት ያበረከቱትን ከፍተኛ አስተዋፅዖ ይገልጻል፡፡

በትዕይንት ሁለት በአራተኛ ደረጃ የተቀመጠው ነጥብም ከ፲፯ኛው እስከ ፲፰ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ በነበረው ጊዜ በግራኝ አሕመድ ወረራ ምክንያት ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናትና ቅዱሳት መጻሕፍት በመቃጠላቸው፣ ሊቃውንቱና ምእመናኑ በግፍ በመጨፍጨፋቸው የተነሣ በሐዋርያዊ አገልግሎቱ ላይ የከፋ ጉዳት መድረሱን ይገልጻል፡፡

በተመሳሳይ መልኩ በዚያ ዘመን ከባዕድ አገር የመጡ የሁለት አካል፣ ሁለት ባሕርይ አማኞች ተፅዕኖ ቢበረታም ተከራክረው መርታት የሚችሉና ለሃይማኖታቸው ሲሉ አንገታቸውን የሚሰጡ አባቶችና እናቶች የተገኙበት ወቅት እንደነበረም ተጠቅሷል፡፡ በዘመነ መሣፍንት በአገራችን ተስፋፍቶ የነበረውን የሁለት አካል ሁለት ባሕርይ አስተሳሰብ ተከትሎ በተፈጠረው የጸጋና የቅብዓት ትምህርት የተከሠተዉን ችግር ለመፍታት ከፍተኛ ጥረት መደረጉም ተገልጿል፡፡

በዚሁ ትዕይንት በአምስተኛ ደረጃ የተቀመጠው ነጥብም ከ ፲፱ኛው እስከ ፳ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ የነበረውን ሐዋርያዊ አገልግሎት የሚያስቃኝ ሲኾን፣ በውስጡም በዘመኑ መጽሐፍ ቅዱስ ከግእዝ ወደ አማርኛ መተርጐሙ፣ በግዳጅ ተይዘው ወደ ሌላ ሃይማኖት ሔደው የነበሩ ምእመናን ወደ ክርስትና መመለሳቸው፣ እንደዚሁም የነመምህር አካለ ወልድ እና መልአከ ሰላም አድማሱ መነሣት ለቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልዕኮ መፋጠን መልካም አጋጣሚ እንደ ነበረ ያስረዳል፡፡

በተጨማሪም ቅዱስ ሲኖዶስ መቋቋሙ፣ የካህናት ማሠልጠኛዎችና መንፈሳውያን ኰሌጆች መመሥረታቸው፣ የሰበካ ጉባኤ መዋቅር መዘርጋቱ፣ ወጣቶች በሰንበት ትምህርት ቤቶችና በማኅበራት አገልግሎት መስጠት መጀመራቸው፣ የምእመናን መንፈሳዊ ተሳትፎ መጨመሩ፣ በውጭዎቹ ክፍላተ ዓለም አብያተ ክርስቲያናት መታነፀቸው እንደዚሁም ቤተ ክርስቲያናችን መገናኛ ብዙኃንና በአፍ መፍቻ ቋንቋ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት መስጠት መጀመሯ በተለይ ፳ኛውን መቶ ክፍለ ዘመን ለሐዋርያዊ ተልዕኮ የተመቸ እንዲኾን ማድረጋቸው ተብራርቶበታል፡፡

በትዕይንት ሁለት የመጨረሻው ርእስ ላይ ደግሞ በአሁኑ ሰዓት የቴሌቭዥንና የሌሎችም መገናኛ ዘዴዎች ሥርጭት አለመኖር፣ በልዩ ቋንቋዎች የሚያስተምሩ ሰባክያንና ካህናት እጥረት እንደዚሁም በየቋንቋው የቅዱሳት መጻሕፍት በበቂ ኹኔታ አለመታተም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት ውሱንነት መገለጫዎች መኾናቸው ተጠቅሷል፡፡

ትዕይንት ሦስት፡- የቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ

ይህ ትዕይንት ቤተ ክርስቲያን ወንጌልን ለማስፋፋት ያሳለፈችውን ተጋድሎ፣ የመናፍቃንን ተፅዕኖና የሰማዕታትን ታሪክ፣ የተዋሕዶ ሃይማኖትን አስተምህሮ ለማስጠበቅ የተደረጉ ልዩ ልዩ ዓለም ዓቀፍና አገር ዓቀፍ ጉባኤያትን በዝርዝር የያዘ ሲኾን፣ በኃይል ሃይማኖቱን ለማጥፋት ይተጉ በነበሩ አካላት ምክንያት ቤተ ክርስቲያን ስላደረገችው ተጋድሎ፣ ስለ ቅዱስ እስጢፋኖስ ሰማዕትነትና በዘመነ ሰማዕታት በክርስቲያኖች ላይ ስለደረሰው መከራ፣ እንደዚሁም በርካታ ክርስቲያኖች በሰማዕትነት ስለማለፋቸው፣ በተጨማሪም ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ተነሥቶ ክርስቲያኖች ዕረፍት ስለማግኘታቸው የሚያትት ዐሳብ ይዟል፡፡

ይህ የትዕይንት ክፍል በአገራችን በኢትዮጵያም እንደ ዮዲት ጉዲት፣ ግራኝ አሕመድ፣ ዐፄ ሱስንዮስ፣ ፋሽስት ጣልያን፣ ያሉ ጠላቶች በቤተ ክርስቲያን ላይ ያደረሱት ጉዳት ተጠቅሷል፡፡ ቀጥሎም የዘመናችን ሰማዕታት በሚል ንዑስ ርእስ ሃይማኖታችንን አንክድም፣ ባዕድ አናመልክም ያሉ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች በ፲፱፻፺፱ ዓ.ም በጂማ ሀገረ ስብከት በበሻሻ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን፤ በቅርቡ በ፳፻፯ ዓ.ም ደግሞ በሊብያ በረሃና በሜዴትራንያን ባሕር ዳርቻ በግፍ የተገደሉ የግብፅ፣ የኢትዮጵያና የሌሎችም አብያተ ክርስቲያናት ሰማዕታትን ይዘክራል፡፡

በቃልም በጽሑፍም በሚበተኑ የሐሰት ትምህርቶች ምክንያት ቤተ ክርስቲያን የፈጸመችውን ተጋድሎ በማውሳት በዚህ የተነሣም ልዩ ልዩ ጉባኤያት መደረጋቸውን ይዘረዝራል፡፡ በዚህ መሠረት ከአይሁድ ወደ ክርስትና ሃይማኖት በመጡትና በቀደሙ ክርስቲያኖች መካከል የልዩነት ትምህርት በመከሠቱ ቅዱሳን ሐዋርያት በ፶ ዓ.ም በኢየሩሳሌም ጉባኤ ማድረጋቸውንና ከዚያ ጊዜ ጀምሮ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እንደ ተመሠርተ ይገልጻል፡፡

በማያያዝም ሦስቱን ዓለም ዓቀፍ ጉባኤያትን (ጉባኤ ኒቅያ፣ ጉባኤ ቍስጥንጥንያ እና ጉባኤ ኤፌሶን) በማንሣት ውሳኔዎቻቸውን አስቀምጧል፤ ይኸውም፡- በ፫፳፭ ዓ.ም ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት አርዮስን ለማውገዝ በኒቅያ ባደረጉት ጉባኤ ጸሎተ ሃይማኖትን (መሠረተ እምነት) ማርቀቃቸውን፤ በ፫፹፩ ዓ.ም ፻፶ው ሊቃውንት መቅዶንዮስን ለማውገዝ በቍስጥንጥንያ ባደረጉት ጉባኤ ወነአምን በመንፈስ ቅዱስ እግዚእ ወማኅየዊ ዘሠረጸ እምአብ፤ ጌታ፣ ማኅየዊ በሚኾን ከአብ በሠረጸ በመንፈስ ቅዱስ እናምናለን የሚለው ሐረግ በጸሎተ ሃይማኖት መካከተቱን፤ በ፬፴፩ ዓ.ም ደግሞ ፪፻ ሊቃውንት ንስጥሮስን አውግዘው በአንዲት የተዋሕዶ ሃይማኖት የሚያጸና ትምህርት ማስተማራቸውን ያትታል፡፡

በተጨማሪም በአገራችን በኢትዮጵያ በሃይማኖት ምክንያት በዐሥራ አምስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የሰንበትን አከባበር አስመልክቶ በቤተ ኤዎስጣቴዎስና በቤተ ተክለ ሃይማኖት መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት ለመፍታት በ፲፬፻፶ ዓ.ም በደብረ ምጥማቅ በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ አማካኝነት ጉባኤ ተደርጎ ሁለቱም ሰንበታት እኩል ይከበሩ የሚል ውሳኔ ስለመተላለፉ፤ ነሐሴ ፲፫ ቀን ፲፰፻፵፮ ዓ.ም በጎንደር ክፍለ ሀገር በደብረ ታቦር ከተማ አምባጫራ በተባለ ቦታ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አባቶች ከቅባትና ከጸጋዎች ጋር የሃይማኖት ጉባኤ አድርገው ጸጋና ቅባቶች ስለመረታታቸው፤ የቅባትና የጸጋ ትምህርት ፈጽሞ ባለመጥፋቱ ግንቦት ፳፩ ቀን ፲፰፻፸፭ ዓ.ም በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት በቦሩ ሜዳ በድጋሜ ከቅባትና ከጸጋዎች ጋር የሃይማኖት ጉባኤ ተደርጎ ቅባትና ጸጋ ተረተው የተዋሕዶ ሃይማኖት ስለመጽናቷ ይገልጻል፡፡

በመጨረሻም የመናፍቃን ሰርጎ ገብነትና የተሐድሶ መናፍቃን ዘመቻዎች የዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተናዎች መኾናቸው በዚህ ትዕይንት ከማስረጃ ጋር ቀርቧል፡፡

ትዕይንት አራት፡- ምን እናድርግ?

ይህ ትዕይንት ደግሞ ምእመናን በዐውደ ርእዩ ከተመለከቷቸውና ከሰሟቸው እውነታዎች በመነሣት የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ከመጠበቅና ድርሻቸውን ከማወቅ አኳያ ልዩ ልዩ ችግሮችን ለመቅረፍ ወደፊት ምን ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው የሚያስረዱ መረጃዎችን አካቷል፡፡

የመጀመሪያው ነጥብ ሐዋርያዊ ተልዕኮን የተመለከተ ሲኾን በርእሱም በ፲፬ አህጉረ ስብከት፣ በ፯፻፳ አጥቢያዎች በተደረገ ጥናት ፫፵፮ አብያተ ክርስቲያናት መዘጋታቸው፣ ፪፻፺፮ቱ አገልጋይ ካህናት እንደሌሉባቸው፣ ፻፷፰ቱ ደግሞ በዓመት/በወር አንድ ጊዜ ብቻ ቅዳሴ የሚቀደስባቸው እንደኾኑ ያስረዳል፡፡

በተያያዘ መረጃ ከ፲፱፻፹፬-፳፻ ዓ.ም ድረስ ባለው ጊዜ ውስጥ ብቻ ሰባት ሚልየን ሰባት መቶ ሰባ ስድስት ሺሕ ሁለት ሃያ ስድስት ምእመናን ወደ ሌሎች ቤተ እምነቶች መወሰዳቸው፣ እንደዚሁም በአዲስ አበባ እና በሌሎች አብያተ ክርስቲያናት መካከል ያልተመጣጠነ የአገልጋዮች ሥርጭት መኖሩ በዚህ ርእስ ሥር ተገልጿል፡፡

በትዕይንት አራት ሌላው ነጥብ የመገናኛ ብዙኃን አጠቃቀም ንጽጽር ሲኾን በንጽጽሩም የግብፅ ኦርቶዶስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፻፴፬ የመካነ ድር፣ ፲፩ የቴሌቭዥን እና ፲ የሬድዮ ሥርጭት ሲኖራት፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ግን ፲፪ የመካነ ድር፣ ፪ የሬድዮ፣ እና ፩ የቴሌቭዥን ሥርጭት ብቻ እንዳላት ተጠቅሷል፡፡

ሁለተኛው የትዕይንት አራት ጭብጥ ደግሞ ገዳማትና የአብነት ትምህርት ቤቶች በመተዳደሪያ ዕጦት፣ በድርቅ፣ በመዘረፍ፣ በበሽታ፣ ወዘተ የመሰሉ ችግር ውስጥ መውደቃቸውን ያስረዳል፡፡

በዚህ ትዕይንት ሦስተኛው ነጥብ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ያልተቋቋሙባቸው አጥቢያዎች መኖርና ያሉትም በቂ አለመኾናቸው፣ የሰባክያነ ወንጌል እጥረትና ግቢ ጉባኤያት ያልተመሠረቱባቸው የትምህርት ተቋማት መኖራቸው ቤተ ክርስቲያን ካጋጠሟት ችግሮች መካከል እንደሚጠቀሱ ይናገራል፡፡

በአራተኛ ደረጃ የተቀመጠው ነጥብ እንደሚያስረዳው የንስሐ አባትና የንስሐ ልጆች ግንኙነት መላላት፣ የምእመናንን መንፈሳዊ የእርስበርስ ግንኙነት (ፍቅር) መቀነስ እንደዚሁም ችግሩ እኔን አይመለከተኝም ብለው የሚያስቡ ምእመናን መበራከት ከቤተሰብና ከማኅበራዊ ኑሮ አኳያ ቤተ ክርስቲያን ያጋጠሟት ችግሮች ናቸው፡፡

በአምስተኛ ደረጃ ከተቀመጠው ነጥብ እንደምንገነዘበው ደግሞ ውጤት ተኮር ዕርዳታ የመስጠት ችግር፣ በልዩ ልዩ ሱስና በአእምሮ ሕመም የተጠቁ ምእመናንን ማገዝ አለመቻሉ፣ ውስን በኾኑ የልማት ሥራዎች ላይ ማተኮር ቤተ ክርስቲያን በማኅበራዊ አገልግሎትና በልማት የጋጠሟት ችግሮች ናቸው፡፡

እነዚህን ከላይ የተዘረዘሩትንና መሰል ችግሮችን ለመቅረፍ በጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ በማኅበረ ቅዱሳን፣ በጽርሐ ጽዮን እና በደጆችሽ አይዘጉ ዓይነት ማኅበራት በስብከተ ወንጌልና በጥምቀት አገልግሎት፣ በሥልጠና፣ እንደዚሁም በሌላ ማኅበራዊና ልማታዊ እንቅስቃሴእየተደረገ ያለው ጥረት የሚበረታታ ቢኾንም ነገር ግን ይህ ብቻ በቂ ስላልኾነ ኹሉም የድርሻውን ቢወጣ የተሻለ ሥራ መሥራትና ለውጥ ማምጣት እንደሚቻል ይጠቁማል፡፡

ይህ ኹሉ ችግር በዚህ ከቀጠለ ቤተ ክርስቲያን ወደፊት በሚሊየን የሚቈጠሩ ምእመናንን፣ አገልጋይ ካህናትን፣ አርአያ የሚኾኑ ገዳማውያን መነኰሳትን ማጣት፤ በቤተሰብ ደረጃም ፍቅር የሌላቸውና ተስፋ የሌላቸው ወጣቶች እንዲበዙ ያደርጋል፡፡

በአጠቃላይ ከላይ የተጠቀሱ ችግሮች በዚሁ ከቀጠሉ ቤተ ክርስቲያን በምጣኔ ሀብትም፣ በማኅበራዊ አገልግሎትና በሌሎችም ዘርፎች ዓቅም የሌላትና ተሰሚነት ያጣች ትኾናለች የሚለው ዐሳብ በትዕይንቱ የተገለጸ ሥጋት ነው፡፡

ከዚህ ቀጥሎ በሥዕል መልክ የተቀናበረው መልእክት እርስዎ የትኛው ነዎት? ያልተረዳ? ያንተ/ያንቺ ድርሻ ነው የሚል? ተወቃቃሽ? ሳይመረምር የሚከተል? ማሰብ ብቻ ሥራ የሚመስለው? ተስፋ የቈረጠ? አልሰማም፤ አላይም፤ አልናገርም የሚል? የሚያወራ፣ የሚተች፣ ግን የማይሠራ? ሲል ይጠይቃል፡፡ የትዕይንቱ ማጠቃለያም ምን እናድርግ? በሚል ርእስ አራት የመፍትሔ አቅጣጫዎችን አስቀምጧል፤

፩. የክርስቶስ አካል በኾነችው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሕያው አካል እንኹን፤

፪. ቤተ ክርስቲያንን በመሰለን ብቻ ሳይኾን በኾነችው እንወቃት፤ እንረዳትም፤

፫. ስለ ቤተ ክርስቲያን ያገባኛል፤ ይመለከተኛል ብለን እንሥራ፤

፬. ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው የኾነውና የማዳን ተግባሩን ኹሉ የፈጸመው ለሰው ልጅ ነው፤

ሰው! ሰው! ሰው!

ኑ፤ አብረን እንሥራ፤ ለውጥም እናመጣለን የሚለው ኃይለ ቃልም እንደማንቂያ ደወል የተቀመጠ መልእክት ነው፡፡

ዐውደ ርእዩ ከነዚህ ዐበይት ትዕይንቶች በተጨማሪ የሕፃናት ትዕይንትም የተካተተበት ሲኾን፣ በዚህ ትዕይንት ለሕፃናት አእምሮ የሚመጥኑ መንፈሳውያን ትምህርቶች ተዘጋጅተውበታል፡፡

በትዕይንቱ ውስጥም የአዳምና የሔዋን ታሪክ፣ ነገረ ድኅነት እና ነገረ ቅዱሳን በሥዕላዊ መግለጫ ቀርቧል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የቤተ ክርስቲያን የዜማ መሣሪያዎችና ንዋያተ ቅድሳት፣ እንደዚሁም ፊደለ ሐዋርያና ሌሎችም የልጆችን ስሜት ሊያስደስቱ የሚችሉ የትዕይንቱ ክፍሎች ተዘጋጅተዋል፡፡ ሕፃናቱም ክፍሉ ውስጥ እየዘመሩ ይማራሉ፤ ይደሰታሉ፡፡

ከሁሉም በተለየ መንገድ ደግም ከቍጥር ፩ አዳራሽ በስተሰሜን አቅጣጫ ካሉት ዛፎች ሥር ጊዜያዊ ጎጆ ቀልሰው የሚገኙት የሁሉም ገባኤያት (የንባብ፣ የዜማ/የድጓ፣ የቅዳሴ፣ የቅኔ፣ የአቋቋም፣ የመጻሕፍትና የአቡሻሕር ጉባኤ ቤቶች) መምህራን ደቀ መዛሙርታቸውን በተግባር ሲያስተምሩመታየታቸው የኤግዚብሽን ማዕከሉን የኹሉም ጉባኤያት መገኛ ገዳም አስመስሎታል፡፡

የንባብ ተማሪዎች ከመምህራቸው ከመምህር ተክለ ጊዮርጊስ ደርቤ እግር ሥር ቁጭ ብለው መጽሐፎቻቸውን በአትሮንሶቻቸው ዘርግተው ተነሽ፣ ተጣይ፣ ወዳቂና ሰያፍ ሥርዓተ ንባብን ለመለየት ይችሉ ዘንድ ተጠንቅቀው ያነባሉ፡፡

የቅዳሴ ደቀ መዛሙርት ከመጋቤ ስብሐት ነጋ፤ የዜማ/የድጓ ደቀ መዛሙርት ደግሞ ከሊቀ ምሁራን ይትባረክ ካሣዬ፤ የዝማሬ መዋሥዕት ደቀ መዛሙርትም ከመጋቤ ብርሃናት ፈንታ አፈወርቅ እግር ሥር ቁጭ ብለው ትልልቅና ባለምልክት የዜማ መጻሕፍቶቻቸውን በአትሮንሶቻቸው ላይ አስቀምጠው በግዕዝ፣ ዕዝልና በዓራራይ በተመሠረተው የቅዱስ ያሬድ ሰማያዊ የዜማ ሥርዓት መሠረት ያዜማሉ፤ መምህራኑም እርማት ይሰጣሉ፡፡

የቅኔ ደቀ መዛሙርትም አንድም ግስ በማውረድ፣ አንድም ከመምህራቸው ፊት ኾነው ቅኔ በመንገርና በማሳረም፣ አንድም መምህራቸው የዘረፉላቸውን ቅኔዎች በመቀጸል ግቢውን አድምቀውታል፡፡ የአቋቋም ደቀ መዛሙርት ደግሞ ከመምህራቸው ከመምህር ዮሐንስ በርሄ ፊት ለፊት ክብ ሠርተው በመቀመጥ በዕለቱ የሚቀጽሉትን ቃለ እግዚአብሔር በጣቶቻቸው እያጨበጨቡ፣ በእግሮቻቸው እያሸበሸቡ ሲያዜሙ የንጋት አዕዋፍን ዝማሬ ያስታውሳሉ፡፡

የአቡሻሕርና የድጓ መምህር የኾኑት መጋቤ አእላፍ ወንድምነው ተፈራም እርጅና ሳይበግራቸው የዘመናት፣ የበዓላት፣ የዕለታትና የአጽዋማት ማውጫ ቀመር የኾውን የባሕረ ሐሳብ ትምህርት ለደቀ መዛሙርታቸው በማስቀጸል ላይ ናቸው፡፡ መምህር ዘለዓለም ሐዲስም የመጻሕፍት ትርጓሜ ደቀ መዛሙርታቸውን ከፊት ለፊታቸው አስቀምጠው ብሉዩንም፣ ሐዲሱንም፣ ሊቃውንቱንም፣ መነኰሳቱንም ለደቀ መዛሙርታቸው ይተረጕማሉ፡፡

ምን ይኼ! ብቻ የብራና መጻሕፍት አዘገጃጀትም የጉብኝቱ አካል ኾኖ ሰንብቷል፡፡ ከዚህ ሌላ ለትዕይንቱ መጨረሻ ከኾነው አዳራሽ ውስጥ ከሚጎበኙ የማኅበሩ ልዩ ልዩ ክፍሎች መካከል አንዱ በኾነው የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮግራም የትዕይንት ክፍል ውስጥ ከጠረፋማ አከባቢዎች የመጡትና የአብነት ትምህርት በመማር ላይ የሚገኙት ሕፃናት ሴቶችና ወንዶች ብትፈልጉ ውዳሴ ማርያም፣ ቢያሻችሁ ደግሞ መልክዐ ማርያም ያነበንቡላችኋል፡፡ ይህም ቤተ ክርስቲያናችን በብሔር፣ በዘር፣ በቀለም፣ በጎሣና በጾታ ሳታበላልጥ የማይነጥፈውን መንፈሳዊ እውቀቷን ለኹሉም እንደምታካፍል አመላካች ነው፡፡

በልማት ተቋማት አስተዳደር ተዘጋጅተው ለሽያጭ የቀረቡት ንዋያተ ቅድሳት (መንበር፣ ልብሰ ተክህኖ፣ አክሊል፣ መጎናጸፊያ፣ ጽንሐሕ/ጽና፣ ቃጭል፣ ወዘተ) እንደዚሁም የቤተ ክርስቲያን የዜማ መሣሪያዎች በሥርዓት ተደርድረው እዩን፤ እዩን፤ ግዙን፤ ግዙን ይላሉ፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍቱም እንደዛው፡፡

ከዐውደ ርእዩ ጎን ለጎን ከምሽቱ 11፡00 ጀምሮ የንባብ፣ የቅዳሴና የሰዓታት፣ የአቋቋምና የዝማሬ መዋሥዕት፣ ባሕረ ሐሳብ (የአቡሻኽር ትምህርት)፣ ቅኔ፣ ትርጓሜ መጻሕፍት፣ ዜማ/ድጓ ምንነታቸውን፣ አገልግሎታቸውን፣ አቀራረባቸውንና ከቅዱሳት መጻሕፍት ጋር ያላቸውን ትስስር የሚያስረዱ ጥናቶች በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ሲቀርቡ ሰንብተዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ እሑድ ግንቦት ፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ ሙስናን ከመዋጋት አንጻር ያለው ሚና እና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ወቅታዊ ፈተናዎችና መፍትሔዎቻቸው በሚሉ አርእስት በዐዲስ አበባ መንገድ ትራንስፖርት ባለሥልጣን አዳራሽ ከቀኑ 8፡00 ጀምሮ ሁለት ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል፡፡

ባጠቃላይ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽ ማዕከል በተዘጋጀው አምስተኛው የማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ተነቧል፤ ተተርጕሟል፤ ተብራርቷል፡፡ በዓለማዊ ጉዳዮች ተጨናንቆ የነበረው የኤግዚብሽን ማዕከሉ በመንፈሳዊ ትምህርትና ጣዕመ ዜማ ደምቆ ለስድስት ቀናት ያህል በመሰንበቱ እጅግ ተደስቷል፡፡ ዐውደ ርእዩ በድጋሜ ቢታይ የሚልም ይመስላል፡፡ ምክንያቱም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአምስተኛው የማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእይ በዐዲስ አበባ ኤግዚአብሽን ማዕከል በግልጽ ታይታለችና፡፡ እርሷን ማየት፣ ትምህርቷንም መስማት፣ ጣዕመ ዜማዋን ማጣጣም እጅግ አስደሳች ነውና፡፡

ከላይ በገለጽነው መልኩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ለምእመናን ሲያስረዳ የነበረው ይህ ዐውደ ርእይ ግንቦት ፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ከምሽቱ 4፡00 ገደማ በሰላም ተጠናቋል፡፡ ይህ ዐውደ ርእይ በእግዚአብሔር ኃይል፣ በቅዱሳን ተራዳኢነት በሚያስደስትና በሚማርክ መልኩ ያለምንም ችግር ተከናውኗል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ርክበ ካህናት

ግንቦት ፲፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ረክብ የሚለው ቃል ተራከበ ተገናኘ ከሚለው የግእዝ ግስ የወጣ ሲሆን ትርጕሙም ማግኛ፣ መገኛ፣ መገናኛ ማለት ነው /ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ገጽ ፰፴፩/፡፡ ርክበ ካህናትም የካህናት መገኛ፣ መገናኛ፣ ጉባኤ (መሰባሰቢያ)፣ መወያያ፣ ወዘተ የሚል ትርጕም ይኖረዋል፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን ቋንቋ ክህነት የሚለው ቃል ከጵጵስና ጀምሮ እስከ ዲቁና ድረስ ያሉትን መዓርጋት የሚያጠቃልል ስያሜ ሲሆን ካህን (ነጠላ ቍጥር)፣ ካህናት (ብዙ ቍጥር) በአንድ በኩል ቀሳውስትን የሚወክል ሆኖ በሌላ በኩል ደግሞ የጳጳሳት፣ የኤጲስ ቆጶሳት፣ የቀሳውስት፣ የዲያቆናት የጋራ መጠሪያ ሆኖ ያገለግላል፡፡ ርክበ ካህናት የቃሉ ትርጕም እንደሚያስረዳው የአባቶች ካህናት ማለትም የብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት (የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት) ጉባኤ ማለት ነው፡፡

በዓሉ በየዓመቱ የትንሣኤ በዓል በዋለ በ፳፭ኛው ቀን ሁልጊዜ በዕለተ ረቡዕ ይዋል እንጂ ወሩና የሚውልበት ቀን ግን የበዓላትንና የአጽዋማትን ቀመር ተከትሎ ከፍና ዝቅ ሊል ይችላል፡፡ የአጽዋማትና የበዓላት ቀመር ከመዘጋጀቱ በፊት ማለትም በቅዱስ ድሜጥሮስ አማካኝነት ዐቢይ ጾም ሰኞ፣ ስቅለት ዓርብ፣ ትንሣኤ እሑድ፣ ርክበ ካህናት ረቡዕ፣ ዕርገት ሐሙስ፣ ጰራቅሊጦስ እሑድ እንዲሆን ከመደረጉ በፊት ርክበ ካህናት ግንቦት ፳፩ ቀን ይውል ነበር /መጽሐፈ ግጻዌ ግንቦት ፳፩/፡፡

ከዚህ በኋላ ግን ርክበ ካህናት በዓለ ትንሣኤ በዋለ በ፳፭ኛው ቀን፣ በበዓለ ሃምሳ እኩሌታ በዕለተ ረቡዕ ይዘከራል፡፡ በያዝነው ዓመት በ፳፻፰ ዓ.ም የትንሣኤ በዓል ከተከበረበት ዕለት (ሚያዝያ ፳፫ ቀን) ጀምሮ ብንቈጥር ፳፭ኛው ቀን ግንቦት ፲፯ ቀን ይሆናል፡፡ በመሆኑም የዘንድሮው ርክበ ካህናት ግንቦት ፲፯ ቀን (በነገው ዕለት) ይውላል ማለት ነው፡፡ ይህ በዓል ከቅዱሳን ሐዋርያት ጀምሮ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሲያስተዳድሩ የቆዩ አባቶቻችን በጋራ በመሰባሰብ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተቀላጠፈ አገልግሎት እንደዚሁም ለምእመናን አንድነትና መንፈሳዊ ዕድገት የሚበጁ መንፈሳውያን መመሪያዎችን የሚያስተላልፉበት ዕለት ነው፡፡

በቅዱስ ዮሐንስ ወንጌል እንደተገለጸው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሞት ከተነሣ በኋላ ለሦስተኛ ጊዜ ተገልጦ ከዐሥራ አንዱ ቅዱሳን ሐዋርያት ጋር ምሳ በልቷል፡፡ ከምሳ በኋላም ጌታችን ቅዱስ ጴጥሮስን ሦስት ጊዜ ጠርቶ ትወደኛለህን? እያለ ከጠየቀው በኋላ እንደሚወደው ምላሽ መስጠቱን ተከትሎ በቅደም ተከተል በጎቼን ጠብቅ፤ ጠቦቶቼን አሰማራ፤ ግልገሎቼን ጠብቅ በማለት የአለቅነት ሥልጣን ሰጥቶታል፡፡ ይህ ምሥጢር ለጊዜው ጌታችን ሐዋርያትን፣ ሰብዐ አርድእትንና ሠላሳ ስድስቱን ቅዱሳት አንስት በአጠቃላይ መቶ ሃያውን ቤተሰብእ እንዲጠብቅና እንዲከባከብ ቅዱስ ጴጥሮስን ማስጠንቀቁን፤ ፍጻሜው ግን የቤተ ክርስቲያን አባቶች (ጳጳሳት) መምህራንንና መላው ሕዝበ ክርስቲያንን እንዲጠብቁና እንዲያስተዳድሩ በእግዚአብሔር መሾማቸውን የሚያስረዳ ትርጕም አለው /ዮሐ.፳፩፥፩-፲፯ (አንድምታ ትርጓሜ)/፡፡

ይህንን የጌታችን ትእዛዝና የሐዋርያትን ሥልጣነ ክህነት መሠረት በማድረግ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በዓመት ሁለት ጊዜ ጉባኤ ያደርጋል፤ የመጀመሪያው ጉባኤ ጥቅምት ፲፪ ቀን (የቅዱስ ማቴዎስ በዓል) ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ ይህ ርክበ ካህናት ነው፡፡ በዚህ ዕለት ቅዱስ ሲኖዶስ በሚያደርገው ጉባኤ የሚተላለፉ መመሪያዎችና የሚጸድቁ ውሳኔዎች ለቤተ ክርስቲያን ዕድገት፣ ለምእመናን አንድነት፣ ለአገር ሰላምና ደኅንነት የሚጠቅሙ ይሆኑ ዘንድ ሁላችንም በጾም በጸሎት እግዚአብሔርን መጠየቅ ይኖርብናል፡፡ አምላካችን ቤተ ክርስቲያናችንንና አባቶቻችንን ይጠብቅልን፤ እኛንም ለአባቶች የሚታዘዝ ልቡና፣ ሓላፊነታችንን የምንወጣበትን ጥበብና ማስተዋሉን ያድለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ፍልሰተ ዐፅሙ ለአቡነ ተክለ ሃይማኖት

ግንቦት ፲፪ ቀን፣ ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤ ግንቦት ፲፪ ቀን በዚህች ቀን ቅዱስ ሚካኤል ሊቀ መላእክት፣ ኢትዮጵያዊው ንጉሥ እስክንድር፣ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ቅዱስ መስቀል፣ ቅዱስ ሚናስ፣ ቅዱስ እስጢፋኖስ፣ የመላልዔል ልጅ ያሬድ፣ እንደዚሁም ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ይታሰባሉ፡፡ በዚህ ዝግጅት የአቡነ ተክለ ሃይማኖትን ፍልሰተ ዓፅም የሚያስታውስ ጽሑፍ ይዘንላችሁ ቀርበናል፤

ስምዑ ወለብዉ ኦ ፍቁራንየ መጽሐፈ ዜናሁ ለክቡር ወቅዱስ ወለብፁዕ ፍቁረ እግዚአብሔር ዘይትነበብ በዕለተ ፍልሰተ ሥጋሁ አመ ፲ወ፪ ለግንቦት ዝ ውእቱ ድሙር ምስለ በዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ወበዓለ ሚካኤል ሊቀ መላእክት ፍቁሩ ለተክለ ሃይማኖት፤ ወዳጆቼ ሆይ፣ የከበረ፣ የተቀደሰ፣ የተደነቀ፣ የእግዚአብሔር ወዳጅ የሚሆን የአባታችን የተክለ ሃይማኖት ክብሩን፣ ገናንቱን የሚናገረውን፣ ዐፅሙ የፈለሰበትን ግንቦት ፲፪ ቀን የሚነበበውን መጽሐፍ አስተውላችሁ ስሙ፤ /ገድለ ተክለ ሃይማኖት ምዕ.፷፪፥፭/፡፡

ተክል ማለት ፍሬያማ ዕንጨት፣ ዛፍ፣ ቅመም፣ ቅጠላ ቅጠል፣ የሚበላ፣ የሚሸተት፣ ገነታዊ ዕፅ፣ እንዲሁም ሕግ ሥርዓት ማለት ነው /ማቴ.15፥13/፡፡ ሃይማኖት ማለት ደግሞ በሀልዎተ እግዚአብሔር፣ እግዚአብሔር የሁሉ አስገኚ መሆኑን፣ በሥላሴ አንድነትና ሦስትነት፣ በቅዱሳን ተራዳኢነት ማመን አምኖም መመስከር ማለት ሲሆን ተክለ ሃይማኖት የሚለው ሐረግም የሃይማኖት ተክል፣ ይኸውም የጽድቅ ፍሬን ያፈራና ከኃጢአት ሐሩር ማምለጫ ዛፍ፣ ምእመናንን በቃለ ወንጌል ያጣፈጠ ቅመም፣ መዓዛ ሕይወቱ የሚማርክ፣ ቢመገቡት ረኃበ ነፍስን የሚያስወግድ ቅጠል፣ የጻድቃን መጠለያ ዕፅ የሚል ትርጕም ይኖረዋል ማለት ነው፡፡ መጽሐፈ ገድላቸውም ተክለ ሃይማኖት ማለት የአብ፣ የወልድ፣ የመንፈስ ቅዱስ ተክል ማለት ነው ሲል ይተረጕመዋል፡፡ አባታችን እርሳቸውም በአሚነ ሥላሴ ጸንተው ሌሎችንም እንዲጸኑና እንዲያምኑ አድርገዋልና፡፡

አቡነ ተክለ ሃይማኖት በ፲፫ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጀመሪያ አካባቢ ከአገራችን ከኢትዮጵያ ምድር ከሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ከኢቲሳ መንደር ከአባታቸው ከካህኑ ጸጋ ዘአብ እና ከእናታቸው እግዚእ ኀረያ አብራክ የተገኙ ቅዱስ አባት ናቸው፡፡ አባታችን ሕይወታቸዉን ሙሉ ለእግዚአብሔር በመስጠት፣ እንደ በሬ ተጠምደው፣ እንደገበሬ ታጥቀው ይህንን ዓለም ንቀው በጾም በጸሎት ተወስነው በብሕትውና ከመኖራቸው በተጨማሪ እንደቅዱሳን ሐዋርያት ወንጌልን በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ የሰበኩ፣ በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ድውያነ ሥጋን በተአምራት፣ ድውያነ ነፍስን በትምህርት የፈወሱ ሐዋርያ ናቸው፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ይህንን ውለታቸውን በማሰብና ከእግዚአብሔር የተሰጣቸውን ቅድስና መሠረት በማድረግ በስማቸው ጽላት ቀርፃ ስታከብራቸው ትኖራለች፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከሚታወሱባቸው በዓላት መካከልም በዛሬው ዕለት የሚከብረው ፍልሰተ ዐፅማቸው አንደኛው ሲሆን ታሪኩንም በአጭሩ እነሆ፤

ጻድቁ አባታችን ምድራዊ ሕይወታቸውን በተጋድሎና በሐዋርያዊ አገልግሎት ከፈጸሙ በኋላ ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ የሚያልፉበት ቀን በተቃረበ ጊዜ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም፣ ከቅዱሳን መላእክት፣ ከቅዱሳን ነቢያትና ከቅዱሳን ሐዋርያት ጋር ወደእርሳቸው በመምጣት የሚያርፉበት ዕለት መድረሱን ነግሯቸው የተጋድሏቸውን ጽናት አድንቆ በስማቸው መታሰቢያ ለሚያደርጉ፣ ለነዳያን ለሚመጸዉቱ ቤተ ክርስቲያን ለሚያሠሩ የምሕረት ቃል ኪዳን ሰጥቷቸው በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡

አቡነ ተክለ ሃይማኖትም የዕረፍታቸው ጊዜ መቃረቡን ባወቁ ጊዜ የመንፈስ ልጆቻቸውን ጠርተው ጌታችን የነገራቸውን ሁሉ አስረድተው አባታዊ ምክርና ተግሣፅ ከሰጧቸው በኋላ ነሐሴ ፳፬ ቀን ከዚህ ዓለም ድካም ዐረፉ፡፡ የመንፈስ ልጆቻቸውም ለአንድ ቅዱስ አባትና ካህን በሚገባ ሥርዓት በማኅሌት፣ በዝማሬና በምስጋና ቀበሯቸው፡፡ ጌታችንም ከእመቤታችንና ከቅዱሳን መላእክት ጋር ተገልጾ ታያቸው፤ ነፍሳቸውንም የጠራሽ፣ ንጽሕት ነፍስ ሆይ ወደእኔ ነዪ ብሎ በክብር ተቀበላት፡፡

በመጽሐፈ ገድላቸው እንደተጠቀሰው ቅዱስ አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት በዚህ ዓለም የኖሩበት ዕድሜ ዘጠና ዘጠኝ ዓመት ከዐሥር ወር ከዐሥር ቀን ነው፡፡ ገድላቸው ዕድሜያቸውን በመከፋፈል፡- በእናት አባታቸው ቤት ፳፪ ዓመት፤ በከተታ ፫ ዓመት፤ በዊፋት ፱ ወር፤ በዳሞት ፲፪ ዓመት፤ በአማራ ፲ ዓመት፤ በሐይቅ ፲ ዓመት፤ በደብረ ዳሞ ፲፪ ዓመት፤ በትግራይ ገዳማት በመዘዋወርና ወደ ኢየሩሳሌም በመመላለስ ፩ ዓመት፤ ዳዳ በሚባል አገር ፩ ወር፤ በአሰቦ ገዳም ፳፱ ዓመት ከ፲ ቀን መቆየታቸውን ይናገራል /ገ.ተ.ሃ.፶፱፥፲፬-፲፭/፡፡

ወደ ፍልሰተ ዐፅማቸው ታሪክ ስንመለስ መጽሐፈ ገድላቸው እንዲህ ሲል ይጀምራል፤ ስምዑ ወለብዉ ኦ ፍቁራንየ መጽሐፈ ዜናሁ ለክቡር ወቅዱስ ወለብፁዕ ፍቁረ እግዚአብሔር ዘይትነበብ በዕለተ ፍልሰተ ሥጋሁ አመ ፲ወ፪ ለግንቦት ዝ ውእቱ ድሙር ምስለ በዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ወበዓለ ሚካኤል ሊቀ መላእክት ፍቁሩ ለተክለ ሃይማኖት፤ ወዳጆቼ ሆይ፣ የከበረ፣ የተቀደሰ፣ የተደነቀ፣ የእግዚአብሔር ወዳጅ የሚሆን የአባታችን የተክለ ሃይማኖት ክብሩን፣ ገናንቱን የሚናገረውን፣ ዐፅሙ የፈለሰበትን ግንቦት ፲፪ ቀን የሚነበበውን መጽሐፍ አስተውላችሁ ስሙ፤ ይኸውም ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤ በዓል ጋር የተክለ ሃይማኖት ወዳጅ ከመላእክት አለቃ ከቅዱስ ሚካኤል በዓል ጋር የተባበረ ነው፡፡ ወንድሞቻችን እንነግራችኋለን፤ እናስረዳችኋለን፡፡ እንደ ዮሐንስና እንደ ነቢዩ ኤርምያስ ከእናቱ ማኅፀን እግዚአብሔር የመረጠው የክቡር አባታችን ዐፅሙ የፈለሰበት ቀን ዛሬ ነው፤ /ገ.ተ.ሃ.፷፪፥፭-፰/፡፡

አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከዚህ ዓለም ከተለዩ በ፶፯ኛው ዓመት የካቲት ፲፱ ቀን ለመንፈስ ልጃቸው ለአባ ሕዝቅያስ ብርሃን ለብሰው በሕልም ተገለጡላቸውና ወዳጄ ሕዝቅያስ ሆይ ሰላም ለአንተ ይሁን! ጌታዬ በኋለኛው ዘመን ከዚህ ሥፍራ ልጆችህ ሥጋህን ያፈልሳሉ ያለኝ ዘመን ደርሷልና ሳትዘገይ ልጆቼን ሁሉ ቅጠራቸውና እስከምፈልስበት ቀን ድረስ ግንቦት ፲፪ ቀን ይሰብሰቡ፡፡ እናንተም በምስጋና በጸሎት መንፈሳዊ በዓልን አድርጉ፡፡ አባቴ ተክለ ሃይማኖት የሚለኝ ሁሉ በዚህች በፍልሰተ ዐፅሜ ቀን ይምጣ፤ መንፈሳዊ በዓልንም ያድርግ፡፡ እኔና ቅዱስ ሚካኤል ከወዳጄ አባ ፊልጶስ ጋር ስለኔ ፍቅር የተሰበሰበውን ሕዝብ ልንባርክ እንመጣለን፤ ከአሏቸው በኋላ ተሠወሯቸው፡፡

አባ ሕዝቅያስም እንደታዘዙት የአባታችሁን ዐፅም ከዋሻው ወደ ታላቁ ቤተ ክርስቲያን ታፈልሱ ዘንድ ኑ፤ ተሰብሰቡ ብለው የአባታችን ወዳጆች በያሉበት ሀገር ሁሉ መልእክት ላኩ፡፡ ምእመናንም ጥሪውን ተቀብለው በዓሉን ለማክበር ከአራቱም አቅጣጫ ተሰበሰቡ፡፡ ዐሥራ ሁለቱ መምህራንም መጡ፤ እነዚህም፡- የወረብ አገሩ አባ አኖሬዎስ፣ የፈጠጋሩ አባ ማትያስ፣ የእርናቱ አባ ዮሴፍ፣ የሞረቱ አባ አኖሬዎስ፣ የመርሐ ቤቴው አባ መርቆሬዎስ፣ የጽላልሹ አባ ታዴዎስ፣ የወገጉ አባ ሳሙኤል፣ የወንጁ አባ ገብረ ክርስቶስ፣ የድንቢው አባ መድኃኒነ እግዚእ፣ የዳሞቱ አባ አድኃኒ፣ የክልአቱ አባ ኢዮስያስ እና የመሐግሉ አባ ቀውስጦስ ናቸው፡፡

እነዚህ መምህራን ከአባ ሕዝቅያስ ጋር በመሆን የአቡነ ተክለ ሃይማኖትን ዐፅም ከዐረፈበት ዋሻ ባወጡት ጊዜ ዐፅማቸው ዕለት የተገነዘ በድን ይመስል ነበር፤ መዓዛውም ሽቱ፣ ሽቱ ይሸት ነበር፡፡ በአባታችን ዐፅም ቀኝና ግራም መስቀል ተተክሎ ነበር፡፡ በዐፅማቸውም ብዙ ድንቅ ተአምራት ተደርገዋል፡፡ ይህንን የአባታችንን ዐፅም አባ ሕዝቅያስና ዐሥራ ሁለቱ መምህራን በሣጥን አክብረው ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ወስደው በመንበሩ ፊት ሦስት ጊዜ አዞሩት፡፡

በዚህች ዕለት አስቀድመው የካቲት ፲፱ ቀን ለአባ ሕዝቅያስ በሕልም እንደነገሯቸው ብፁዕ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከቅዱስ ሚካኤልና ከአባ ፊልጶስ ጋር ወደ ቤተ ክርስቲያኑ መጥተው ዐፅማቸው እስኪያረፍ ድረስ ከመንበሩ ተቀምጠው ቆይተው ዐፅማቸው ካረፈ በኋላ የተሰበሰበውን ሕዝብ ባርከው በክብር ወደ ሰማይ ዐረጉ፡፡ መምህራኑና ምእመናኑም በዓሉን በታለቅ ደስታ አክብረው በሰላም ወደየቤታቸው ተመለሱ፡፡ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ፍልሰተ ዐፅም ከዋለበት ዕለት ጋር ርክበ ካህናት አብሮ መዋሉ በዓሉን ልዩ ድምቀት ሰጥቶት ነበር /ገ.ተ.ሃ.፷፭፥፩-፳፬/፡፡

ከዚያ ዘመን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ በታላቁ ገዳም በደብረ ሊባኖስ ቅዱሳን ፓትርያሪኮች፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትና በርካታ ምእመናን እየተሰበሰቡ በዓሉን በድምቀት ያከብራሉ፡፡ የብፁዕ አባታችን ዐፅማቸው በፈለሰበት ዕለት ዐሥራ ሁለቱ መምህራን እና በርካታ ምእመናንን እንደተሰበሰቡ ሁሉ እኛንም እግዚአብሔር አምላካችን በኢየሩሳሌም ሰማያዊት ይሰብስበን፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፤ የአቡነ ተክለ ሃይማኖትና የመንፈስ ልጆቻቸው ጸሎት፣ ረድኤትና በረከት ለዘለዓለሙ ይጠብቀን፡፡

ምንጭ፡-

ገድለ ተክለ ሃይማኖት፣ ፲፱፻፹፱ ዓ.ም፤ አዲስ አበባ፡፡

መጽሐፈ ስንክሳር፣ ግንቦት ፲፪ ቀን፡፡

ቅዱስ ያሬድ ኢትዮጵያዊ

ግንቦት ፲፩ ቀን፣ ፳፻፰ ዓ.ም

ዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤ በየዓመቱ ግንቦት ፲፩ ቀን ከሚታወሱ ቅዱሳን መካከል የእመቤታችን እናት ቅድስት ሐና፣ ቅድስት ታውክልያ፣ ቅዱስ በፍኑትዩስ፣ አባ አሴር፣ ቅዱስ ያሬድ፣ ብፅዕት አርሴማ፣ ቅድስት ኤፎምያ፣ ቅድስት አናሲማ፣ ቅድስት ሶፍያ፣ አባ በኪሞስ፣ አባ አብላዲስ እና አባ ዮልዮስ ተጠቃሾች ሲሆኑ፣ በዛሬው ዝግጅታችን የቤተ ክርስቲያን እንዚራ፣ የኢትዮጵያ ብርሃን እየተባለ የሚጠራውን የቤተ ክርስቲያናችን ድምቀት፣ የአገራችን ኩራት የሆነውን የጥዑመ ልሳን፣ ኢትዮጵያዊ ማኅሌታይ የቅዱስ ያሬድን ታሪክ በአጭሩ ይዘንላችሁ ቀርበናል፤

በ፭፻፭ ዓ.ም በአገራችን በኢትዮጵያ በአክሱም ከተማ ከአባቱ ከአብዩድ (ይስሐቅ) እና ከእናቱ ታውክልያ (ክርስቲና) አንድ ቅዱስ ተገኘ፤ ይኸውም ቅዱስ ያሬድ ነው /ገድለ ቅዱስ ያሬድ/፡፡ ቅዱስ ያሬድ ዕድሜው ለትምህርት ሲደርስ ከአጎቱ ከአባ ጌዴዎን ዘንድ ትምህርት ሊማር ቢሔድም ለበርካታ ዓመታት ትምህርት ሊገባው አልቻለም ነበር፡፡ በዚህም የተነሣ መምህሩ ይገርፉት፣ ይገሥፁት ነበር፡፡ እርሱም ከትምህርቱ ክብደት ባለፈ የመምህሩ ተግሣፅ ሲበረታበት ጊዜ ከአባ ጌዴዎን ቤት ወጥቶ በመሸሽ ላይ ሳለ ደክሞት ከአንድ ዛፍ ሥር ተቀመጠ፡፡

ከዛፉ ሥር ተጠልሎ ሳለ አንድ ትል ፍሬውን ለመመገብ ወደ ዛፉ ሲወጣ፣ ነገር ግን መውጣት ስለተሳነው በተደጋጋሚ ሲወድቅ ቆይቶ ከብዙ ሙከራ በኋላ ከዛፉ ላይ ሲወጣ፣ ፍሬውንም ሲመገብ ይመለከታል፡፡ ቅዱስ ያሬድ የትሉን ትጋት ከአየ በኋላ እርሱም በተደጋጋሚ ሙከራ ቢያደርግ የከበደው ምሥጢር እንደሚገለጽለት በማመን ወደ መምህሩ ተመልሶ ይቅርታ ከጠየቀ በኋላ ትምህርቱን እንደገና መቀጠል ጀመረ፡፡ እግዚአብሔርን በጸሎት እየተማጸነ ትምህርቱን ሲከታተል ከቆየ በኋላ በአጭር ጊዜ ውስጥ ልቡናው ብሩህ ሆኖለት የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት ትርጓሜን አጠናቆ መዓርገ ዲቁና ተቀበለ፡፡

እግዚአብሔርም የክብር መታሰቢያ ሊያቆምለት ወዷልና ከኤዶም ገነት ሦስት አዕዋፍን ልኮ በሰው አንደበት እንዲያናግሩት አደረጋቸው፡፡ እነርሱም ካናገሩት በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት አወጡትና በዚያም የሃያ አራቱን ካህናተ ሰማይ (ሱራፌል) ማኅሌት ተማረ፡፡ ወደ ምድርም ተመልሶ በአክሱም ጽዮን በሦስት ሰዓት ገብቶ በታላቅ ቃል፡- ሃሌ ሉያ ለአብ ሃሌ ሉያ ለወልድ ሃሌ ሉያ ለመንፈስ ቅዱስ ቀዳሚሃ ለጽዮን ሰማየ ሣረረ ወበዳግም አርአዮ ለሙሴ ዘከመ ይገብር ግብራ ለደብተራ፤ ለአብ ምስጋና ይገባል፤ ለወልድ ምስጋና ይገባል፤ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይገባል፡፡ የጽዮን ደገኛዋ ሰማይን ፈጠረ፡፡ ዳግመኛም እንዴት መሥራት እንዳለበት የድንኳንን አሠራር ለሙሴ አሳየው፤ አስተማረው እያለ በዜማ እግዚአብሔርን አመሰገነ፡፡ የቅዱስ ያሬድን ድምፅ የሰሙ ሁሉ ጳጳሳቱና ነገሥታቱ ሳይቀሩ ካህናቱም ምእመናኑም ወደርሱ ተሰብስበው ሲሰሙት ዋሉ፡፡ ይህንንም ምስጋና አርያም ብሎ ጠራው፤ ይኸውም በዜማ ትምህርት ቤት ከቃል ትምህርቶች አንደኛው ሆኖ በመሰጠት ላይ ይገኛል፡፡

መጽሐፈ ስንክሳር ይህንን ሊቅ፡- አምሳሊሆሙ ለሱራፌል፤ የሱራፌል አምሳላቸው ይለዋል፡፡ ከመላእክት ወገን የሆኑት ሱራፌል እግዚአብሔርን ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እያሉ በመንበሩ ፊት ቆመው እንደሚያመሰግኑ ሁሉ ቅዱስ ያሬድም ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እያለ በመላእክት ቋንቋ እግዚአብሔርን አመስገኗልና፤ ደግሞም የተማረው ከእነርሱ ነውና የሱራፌል አምሳላቸው ተባለ፡፡ እርሱም፡- ሃሌ ሉያ ዋይ ዜማ ዘሰማዕኩ በሰማይ እመላእክት ግናይ እንዘ ይብሉ ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር መልዐ ሰማያተ ወምድረ ቅድሳተ ስብሓቲከ፤ ምስጋና ለእግዚአብሔር ይሁን! ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር፤ የምስጋናህ ስፋት ሰማይና ምድርን መላ፤ /ኢሳ.፮፥፫/እያሉ ሲያመሰግኑ ከመላእክት የሰማሁት ምስጋና ምንኛ ድንቅ ነው? በማለት ዜማውን የተማረው ከመላእክት መሆኑን በድርሰቱ መስክሯል፡፡

ከዚያ በኋላ በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ከዓመት እስከ ዓመት ድረስ በየክፍለ ዘመኑ በክረምትና በበጋ፣ በመጸውና በጸደይ፣ በአጽዋማትና በሰንበታት፣ እንዲሁም በመላእክት፣ በጻድቃን፣ በሰማዕታት፣ በደናግል በዓላት የሚደረስ ቃለ እግዚአብሔር በሦስት ዜማዎች ማለትም በግእዝ፣ በዕዝልና በአራራይ ደረሰ፡፡ የሰው ንግግር፣ የአዕዋፍ፣ የእንስሳትና የአራዊት ጩኸት ሁሉ ከነዚህ ከሦስቱ ዜማዎች እንደማይወጡ መጽሐፈ ስንክሳር ይናገራል፡፡

በአንዲት ዕለት ቅዱስ ያሬድ ከብሉይና ከሐዲስ፣ እንደዚሁም ከሊቃውንትና ከመነኮሳት የተውጣጣውን መንፈሳዊ ድርሰቱን በዘመኑ ከነበረው ከንጉሥ ገብረ መስቀል ፊት ቆሞ ሲዘምር ንጉሡ በድምፁ በመማረኩ የተነሣ ልቡናው በተመስጦ ተሠውሮበት (የሚያደርገዉን ባለማወቁ) የቅዱስ ያሬድን እግር በጦር ወጋው፡፡ ከቅዱስ ያሬድ እግር ደምና ውኃ ቢፈስስም ነገር ግን ማኅሌቱን እስኪፈጽም ድረስ ሕመሙ አልተሰማውም ነበር፡፡

ንጉሡም ያደረገዉን ሁሉ ባወቀ ጊዜ ደነገጠ፤ ጦሩንም ከእግሩ ነቅሎ ስለፈሰሰው ደምህ ዋጋ የምትፈልገዉን ሁል ለምነኝ እያለ ተማጸነው፡፡ ቅዱስ ያሬድም ላትከለክለኝ ማልልኝ ብሎ ቃል ካስገባው በኋላ ወደ ገዳም ሔዶ ይመነኩስ ዘንድ እንዲፈቅድለትና እንዲያሰናብተው ለመነው፡፡ ንጉሡም ከመኳንንቱ ጋር እጅግ አዘነ፤ ተከዘ፡፡ ከእርሱ እንዲለይ ባይፈልግም ነገር ግን መሐላዉን ማፍረስ ስለከበደው እያዘነ አሰናበተው፡፡

ከዚያም ቅዱስ ያሬድ በአክሱም ጽዮን ቤተ መቅደስ በታቦተ ጽዮን ፊት ቆሞ፡- ቅድስት ወብፅዕት ስብሕት ወቡርክት ክብርት ወልዕልት አንቀጸ ብርሃን መዐርገ ሕይወት፤ ፈጽሞ የከበርሽና የተመሰገንሽ፣ ከፍ ከፍም ያልሽ፣ የብርሃን መውጫ የሕይወት ማዕረግ የሆንሽƒ‚ƒƒ‚ እያለ አንቀጸ ብርሃን የተባለውን የእመቤታችን ምስጋና እስከ መጨረሻው ድረስ ደረሰ፡፡ ይህንን ጸሎት ሲያደርስም አንድ ክንድ ያህል ከመሬት ከፍ ብሎ ይታይ ነበር፡፡ከዚህ በኋላ ወደ ሰሜን አገር ሔዶ (ሰሜን ተራሮች አካባቢ) በጾም በጸሎት ተወስኖ ሥጋውን እጅግ እያደከመ ኖሮ ገድሉን በዚያው ፈጸመ፡፡ እግዚአብሔርም ስሙን ለሚጠራ፣ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው፤ ከዚያም በሰላም ዐረፈ፡፡ /ምንጭ፡- መጽሐፈ ስንክሳር፣ ግንቦት ፲፩/

የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት በገድለ ቅዱስ ያሬድ ላይና በመጽሐፈ ስንክሳር እንደመዘገቡልን ግንቦት ፲፩ ቀን ቅዱስ ያሬድ ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ ያረፈበት ቀን ነው፤ እዚህ ላይ ግን አከራካሪ ጉዳይ አለ፤ ይኸውም አንደኛው ቅዱስ ያሬድ ሞቶ ተቀብሯል የሚል ሲሆን፣ ሌላኛው ደግሞ ቅዱስ ያሬድ እስከነ ነፍሱ ተሠወረ እንጂ አልሞተም የሚል ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድ ሞተ የሚሉ ወገኖች ከሚጠቅሷቸው ማስረጃዎች ውስጥ በመጽሐፈ ስንክሳር፡- ወበዛቲ ዕለት አዕረፈ ያሬድ ማኅሌታይ፤ በዚህች ዕለት ማኅሌታይ ያሬድ ዐረፈ፤ እና ወእምዝ አዕረፈ በሰላም፤ ከዚህ በኋላ በሰላም ዐረፈ የሚሉት ሐረጋት የሚገኙ ሲሆን፣ ተሠወረ የሚሉት ደግሞ እዚያው ስንክሳሩ ላይ፡- ወእምዝ ሖረ ሀገረ ሰሜን ወነበረ ህየ ወፈጸመ ገድሎ፤ ከዚህ በኋላ ወደ ሰሜን አገር ሒዶ ገድሉን በዚያ ፈጸመ፤ ተብሎ የተገለጸውን እንደማስረጃ ይጠቅሳሉ፡፡

በእርግጥ ቃሉን በትኩረት ለተመለከው ሰው ዐረፈ ማለት ሞትን ብቻ ሳይሆን እንደነ ሄኖክ ከዚህ ዓለም ጣጣና እንግልት ተለይቶ በሕይወት እያሉ (ሳይሞቱ) ተሠውሮ መኖርንም ያመለክታል፡፡ ገድሉን በሰሜን አገር ፈጸመ የሚለውም መሠወሩን ብቻ ሳይሆን መሞቱንም ሊያመለክት ይችላል የሚሉም አሉ፡፡ ነገር ግን የቤተ ክርስቲያን መምህራን እንደሚያስተምሩን እነእገሌ ቀበሩት የሚል ቃል ስለማይገኝ ቅዱስ ያሬድ ተሠወረ እንጂ ሞተ ተብሎ አይነገርለትም፡፡ ለዚህም ማስረጃ እርሱ በተሠወረበት ተራራ እስከ አሁን ድረስ የከበሮ (የማኅሌት) ድምፅ ይሰማል፤ የዕጣን መዓዛ ይሸታል፡፡ ይህም ቅዱሱ ከሰው ዓይን ተሠውሮ እግዚአብሔርን እያመሰገነ እንደሚገኝ አመላካች ነው፡፡

የቅዱስ ያሬድ ድርሰቶችም ለቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን ለአገርም ድንቅና ወደር የሌላቸው ሀብቶች ናቸው፡፡ በመሆኑም የዜማ ድርሰቶቹ (ድጓ፣ ጾመ ድጓ፣ ምዕራፍ፣ ዝማሬ፣ መዋሥዕት) እንደሌሎቹ ቅርሶች ሁሉ በዩኔስኮ እንዲመዘገቡ የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ ከፍተኛ ርብርብ በያደርጉ መልካም ነው፡፡ በቅዱስ ያሬድ ዜማ የሚደምቀው በዓለ ጥምቀት በዩኔስኮ ሲመዘገብ ዜማውን ከበዓሉ ለይቶ ማስቀረት የታሪክ ተወቃሾች ያደርገናልና ሁላችንም እናስብበት እንላለን፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፤ እኛንም በአባታችን በቅዱስ ያሬድ ጸሎት ይማረን፡፡ በረከቱም ከእኛ ጋር ለዘለዓለም ትኑር፤ አሜን፡፡

የማኅበሩ መልእክት

የካቲት 14 ቀን 2008 ዓ.ም

በሚመስለን ከተጨባጩ፤ በመላምትም ከእውነታው አንጣላ

በአሁኑ ወቅት በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ባሉ አማኞችም ሆነ በሀገራችን ውስጥ ባሉ ዜጎች መካከል ልዩነቶችን አጉልቶ በማሳየት የመጠቃቃትን ስሜት ለመፍጠር የሚጣጣሩ መኖራቸውን ለመታዘብ የተለየ ጥናት የሚጠይቅ ነገር አይደለም፡፡ በተለያየ መንገድ የምንሰማቸው ዜናዎችና ወሬዎችም ከዚህ የራቁ አይደሉም፡፡ ምንም እንኳ ልዩነት ተፈጥሮአዊ እስከሚመስል ድረስ ከጥንት ጀምሮ የነበረ ቢሆንም ውጤቱ ግን እንደየዘመኑ የማኅበረሰብና የተቋማት መሪዎች አቅም እንደ ማኅበረሰቡም ግንዛቤ ይለያያል፡፡

የማኅበረሰብና የተቋማት መሪዎች ለሚመሩት ማኅበረሰብ እንደ አንድ ጤነኛ ሰው ጭንቅላት የሚታዩ ሲሆን የተለያዩት የማኅበረሰብ አካላትን በአንድ አካል ውስጥ እንዳሉ ብልቶች በማዋሐድና ጤንነታቸውንም በመጠበቅ ልክ እንደ አንድ ጤናማ ሰው ሙሉ ጤነኛ አካል አድርገው ይመሯቸዋል፡፡ ውሕደታቸው፣ መናበባቸው፣ መረዳዳታቸውና መተባበራቸውም ልክ በአንድ ጤነኛ ሰው እንዳሉ የተለያዩ ብልቶች ይሆንና ከልዩነታቸው የሚጎዱ ሳይሆን በልዩነታቸው የሚያጌጡና የሚጠቀሙ ይሆናሉ፡፡ የማኅበረሰቡ አካላትም እንደዚያው ጤነኛ ብልቶች ከሆኑ ለራሳቸውም ሆነ ብልት ለሆኑለት አካል ጠቃሚዎች ይሆናሉ፡፡ በሽተኞች ሲሆኑም ፈጥነው ሕክምና ካላገኙና ካልዳኑ ጉዳታቸው በእነርሱ ሳይወሰን መላው አካልን ይጎዳሉ፤ ሕመሙ ሲከፋም የጋራ ሞትን ያስከትላሉ፡፡ ስለዚህም በሰውነታችን እንደምናየው፣ «አፍንጫ ሲመታ ዓይን ያለቅሳል´ ከሚሉት ዓይነት አባባሎችም እንደምንረዳው እያንዳንዱ ብልት ለሌላው ጤንነት የድርሻውን ይወጣል፡፡ ይህ መሆን ካልቻለ ለሁሉም የሚደርስባቸው ጉዳት ታላቅ ይሆናል፡፡ ብልቶች ከተለያዩ ውጤቱ የአካል መለያየትና የሁሉም የሰውነት አካል የጋራ ሞት እንደሆነ የታወቀ ነውና፡፡

ኦርቶዶክሳዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ስለ ሰው ልጆች ማኅበራዊ ሕይወት ጤንነትም ሆነ በውስጧ ስላለው መንፈሳዊ አገልግሎት ልጆቿን ከምታስተምርበትም ሆነ ዓለምን ከምትመክርበት፤ ተቋማዊ ሂደቷንም ከምትመራባቸው መንፈሳዊ አስተምህሮዎችና መርሆዎች አንዱና ዋናው ይህንኑ የሚከተል እንደሆነ ቅዱስ መጽሐፍ ይመሰክራል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለቆርንቶስ ምእመናን በላካት የመጀመሪያይቱ መልእክት ላይ የሚከተለውን ብሏል፡-

አካልም አንድ እንደ ሆነ ብዙም ብልቶች እንዳሉበት ነገር ግን የአካል ብልቶች ሁሉ ብዙዎች ሳሉ አንድ አካል እንደ ሆኑ፥ ክርስቶስ ደግሞ እንዲሁ ነው፤ አይሁድ ብንሆን የግሪክ ሰዎችም ብንሆን ባሪያዎችም ብንሆን ጨዋዎችም ብንሆን እኛ ሁላችን በአንድ መንፈስ አንድ አካል እንድንሆን ተጠምቀናልና። ሁላችንም አንዱን መንፈስ ጠጥተናል። አካል ብዙ ብልቶች እንጂ አንድ ብልት አይደለምና። እግር፦ እኔ እጅ ስላልሆንኩ የአካል ክፍል አይደለሁም ብትል፥ ይህን በማለትዋ የአካል ክፍል መሆንዋ ይቀራልን? ጆሮም፦ እኔ ዓይን አይደለሁምና የአካል ክፍል አይደለሁም ቢል፥ ይህን በማለቱ የአካል ክፍል መሆኑ ይቀራልን? አካል ሁሉ ዓይን ቢሆን መስማት ወዴት በተገኘ? ሁሉም መስማት ቢሆን ማሽተት ወዴት በተገኘ? አሁን ግን እግዚአብሔር እንደ ወደደ ብልቶችን እያንዳንዳቸው በአካል አድርጎአል። ሁሉም አንድ ብልት ቢሆንስ አካል ወዴት በሆነ? ዳሩ ግን አሁን ብልቶች ብዙዎች ናቸው አካል ግን አንድ ነው። ዓይን እጅን፦ አታስፈልገኝም ልትለው አትችልም፥ ወይም ራስ ደግሞ እግሮችን፦ አታስፈልጉኝም ሊላቸው አይችልም። /1ኛ ቆሮ 12 ፥ 12 – 21/

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በሰፊው ግልጽ አድርጎ እንዳስቀመጠው፡- በሀገራችን በኢትዮጵያ የምንገኝ ሁላችን ራሳችን ለራሳችን የሰጠነው የተለያየ ማንነት ቢኖርም ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለው ልዩነታችን እንደ ዓይን እና ጆሮ፣ እጅ እና እግር ወይም እንደ ልብና ኩላሊት ከመሆን ያለፈ አይደለም፡፡ አንዳንዶቻችን የተስማማንን ማኅበረሰባዊ የማንነት መለያዎች ለራሳችን ብንሰጥና በዚያም መለያ ብንመደብ እንኳ ካወቅንበት ይህ ልዩነታችን በአንድ አካል ውስጥ እንዳሉ ብልቶች በየተሰጠን ጸጋ፣ ሙያና ችሎታ የምንጠቃቀምበት የምንከባበርበት እንጂ የሚጎዳን ሊሆን አይችልም፡፡ በመጀመሪያ በተፈጥሮ ሰው ሆነን በመፈጠራችን ልዩነት የሌለን መሆኑን ማስታወስ ነው፡፡ ያም ባይሆን ደግሞ ልዩነትን እንደተፈጥሮ ጸጋ ብንወስደው እንኳ ይህ የሚጠቅም እንጂ የሚጎዳ አይደለም፡፡

ቅዱሱ ሐዋርያ በደንብ እንደገለጸው ዓይን እጅን አታስፈልገኝም ልትለው የማትችለውን ያህል በሀገራችንም አንዱ ሌላውን የኅብረተሰብ ክፍል አታስፈልገኝም ቢለው ተፈጥሮአዊ አይደለምና ተጠቃሚ ሊሆን አይችልም፡፡ ምንም እንኳ ጥርስ ምላስን እንደሚነክሰው፣ እግርም እግርን እንደሚረግጠው ወይም እጅ እጅን እንደሚያቆስለው ካለበለዚያም ጣትም ዓይንን እንደሚያስለቅሰው ሁሉ በቀደመው ታሪካችን አልፎ አልፎ የእርስ በርስ ወይም የብልት ከብልት መጎዳዳት ተከስቶ የነበረ መሆኑ ቢታወቅም ይህም ከልዩነት የተነሣ ብቻ ሳይሆን ከተፈጥሮም ጠፍቶ የማያውቅ በመሆኑ በብልቶቻችን ዘንድ በእንደዚህ ዓይነት ምክንያት እስከመጨረሻው መለያየት ሆኖ እንደማያውቀው ሁሉ ራሳችን ሆን ብለን ካልፈቀድንለት በስተቀር እኛንም እንዲህ ዓይነት ታሪካዊ ምክንያቶች ሊለያዩን አይችሉም፡፡ ምክንያቱም እጅ ዓይንን ብቻ ሳይሆን እጅንም የሚጎዳ መሆኑ እንዲህ ያለ ጉዳት የእርስ በርስ መሆኑንም እንድንረዳ ፈጣሪ የሰጠን የማስተዋል ወይም የመመርመሪያ መንገድ ይመስለናልና፡፡

ስለዚህም ታሪካዊ ክስተቶችን እያነሣንና እየጣልን በቁስል ላይ ቁስል ከምንጨምር ይልቁንም በአንድ አካል እንዳሉ ብልቶች የቆሰለውን የማዳን እንጂ ያልቆሰለውን የማቁሰልን ተግባር ልንጸየፈው ይገባናል፡፡ ምንአልባት በሰዎች ዘንድ ቅዱሱ ሐዋርያ እጅን ወይም እግርን አታስፈልጉኝም የሚል ዓይን ወይም ጆሮ ሊኖር አይችልም እንዳለው በእኛም ዘንድ ይህ ሊሆን አይገባውም፡፡ መስሎን የምንል ሰዎች ካለንም መናገር በመቻላችንና ይህንኑንም አብዝተን በማለታችን ምክንያት ግን የአካል ክፍል አድርገን ያልቆጠርነው ክፍል አካል አለመሆን አይችልም፡፡ እንኳን በሌሎቹ በራሳችንም ላይ ቢሆን እንዲህ ያለው ነገር የምንናገረውን ያህል ቀላል፣ ጉዳቱም ለሌሎቹ ብቻ ሊሆን አይችልምና ደጋግሞ መመርመሩ ነገሮችንም በእውነት ማጤኑ በእጅጉ አስፈላጊ ይመስለናል፡፡

ስለዚህም ነገሮችን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በገለጸውና የሕይወታችን መመሪያ በሆነው መንገድ እንድንመረምራቸውና በሌሎች አካላትም ይሁን በራሳችን ስሜት ተገፋፍተን ለእኛ ምንአልባትም ጠቃሚ ከመሰለን፣ ነገር ግን ደግሞ በእውነት ጠቃሚ ካልሆነው ነገር እንድንድንና አንዳችን ለሌላችን ጠቃሚዎች እንድንሆን የሚከተሉትን ነገሮች እንድናጤናቸው ያስፈልጋል፡፡

1.የሚመስለንን አንመነው፤ ይልቁንም እንመርምረው፡፡

በቅዱስ መጽሐፍ ተደጋግመው ከተገለጹልን ነገሮች አንዱ የሚመስለንን ነገር ይዘን እንዳንቀመጥ ነው፡፡ እንኳን እንዳሁኑ አስመሳይ በበዛበት ዓለም ውስጥ እየኖርን ቀርቶ በንጽሕና በቅድስና በሚኖሩትም ዘንድ ይህ ፈተና የሚሆን መሆኑን ዐውቀን እንድንጠነቀቅ ብዙ ጊዜ ተጽፎልናልና፡፡ ለምሳሌ ያህል በሃይማኖት ዐዋቂዎች መምህራን ነን ብለው ከሚኖሩት ብዙዎቹ የራሳቸው መንገድ ብቻ ትክክል መስሏቸው ከኖሩ በኋላ ጌታ አላውቃችሁም ሲላቸው እነርሱ እንደሚያውቁትና ራሱንም ሳይቀር በአንተ ስም አይደለም ወይ ይህን ተአምር ያደረግን እያሉ እንደሚከራከሩትም ራሱ ጌታችንም አስቀድሞ አሳስቧል /ሉቃ 13 ፥ 25/፡፡ ከዐሥሩ ደናግልም አምስቱ ማሰሮ በመያዛቸው ብቻ የሚጠቀሙ ይመስላቸው እንደነበር ነገር ግን በማሰሮው ውስጥ የሚያስፈልገውን ዘይት ይዘው ባለመገኘታቸው የሠርጉ ታዳሚ ሳይሆኑ እንደቀሩ ተጽፎልናል /ማቴ 25 ፥ 1-10/፡፡ እንዲሁም መክሊቱን የቀበረውም ሰው የተሻለ ያደረገና በጌታው ዘንድ የበለጠ የሚመሰገን ይመስለው ነበር፤ ነገር ግን ይህ ሳይሆን ቀረ፡፡ /ማቴ 25 ፥ 14-30/፡፡ እኒህ ሁሉ የገጠማቸው ከመሰላቸው በተቃራኒው ነው፡፡ ምክንያቱም በመሰላቸው እንጂ በሚሆነውና በእውነታው አልኖሩምና፡፡

ከላይ በጠቀስነው መልእክትም ላይ ቅዱስ ጳውሎስ ነገር ግን ደካሞች የሚመስሉ የአካል ብልቶች ይልቁን የሚያስፈልጉ ናቸው፤ ከአካልም ብልቶች ያልከበሩ ሆነው የሚመስሉን በሚበዛ ክብር እናለብሳቸዋለን፥ በምናፍርባቸውም ብልቶቻችን ክብር ይጨመርላቸዋል /1ኛ ቆሮ 12 ፥ 22 – 23/ ሲል እንደገለጸው የሚመስለን ከእውነታው ብዙ ጊዜ ሊራራቅ እንደሚችል ማሰብና መመርመር ከነባራዊ እውነትም ጋር መታረቅና መስማማት ለሁላችንም ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ነገሮችን በአግባቡ ሳይመረምሩና በአግባቡ ሳያጠኑ ወይም በስሜታቸው ተገፋፍተው የሚቀሰቅሱንን እየሰማን ለራሳችን ባለንና በሰጠነው ማንነት ላይ ተመሥርተን ሌሎች የማያስፈልጉ ከመሰለን በእጅጉ እንሳሳታለን፡፡ እንደ እውነታው ከሆነ ሁላችንም ብንሆን አንዳችን ለሌሎቻን የምናስፈልግና የምንጠቅም መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል፡፡

ነገሩን በጽድቅና በኩነኔ ብቻ ሰፍረን የእኛ ያጸድቃል የሌሎች ያስኮንናል ብለን ብናምን እንኳ በዚች ምድር ላይ ለመኖር ግን አንዱ ለሌላው አስፈላጊ መሆኑ ሊታበል አይችልም፡፡ ምክንያቱም የሃይማኖት ውጤቱ በሰማይ (በፈጣሪ በሚሰጥ ፍርድ) የሚገለጽ በመሆኑ ብቻ ሳይሆን በምድርም ፈጣሪ ለሁሉም ፀሐይ በማውጣቱ ዝናም በማዝነሙና ሁሉንም በመመገቡ የፈቀደለትን እኛ በጉልበትና በግጭት ልናጠፋው እንደማይገባን ብቻ ሳይሆን እንደማንችልም መረዳት አስፈላጊ ነውና፡፡ ስለዚህም ልዩነትን ምክንያት በማድረግ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የሚፈጸሙ አብያተ እምነቶችን ማቃጠል፤ በአንድ አካባቢ በቁጥር አነስ ያሉና የተለየ ማንነት ያላቸውን ማሳደድ፣ ማፈናቀልና መጉዳት ለጊዜው ማሸነፍ ቢመስልም እውነታው ተቃራኒው ሊሆን እንደሚችል ማሰብና በመከባበርና በመረዳዳት መኖሩ ሊጠቅም እንደሚችል ማስተዋሉ በእጅጉ ያስፈልገናል፡፡ ስለዚህም በሃይማኖትና በብሔር ከመጣላት ራስን ብቻም የተለየ አስፈላጊና ጠቃሚ ሌላውን ደግሞ ጎጂና የማይረባ፣ አንዳቻንን አሳቢ ሌላውን ማሰብ የማይችል፤ አንዱን ተሸካሚና ሌላውንም ሸክም አስመስለው ከሚያቀርቡ የልዩነት ሐሳቦች ራስን ማቀብ በእጅጉ ያስፈልጋል፡፡ የሚመስለን ሁሉ እውነታ ላይሆን ይችላልና፡፡

ስለዚህም አሁን በሀገራችን ውስጥ ያለው የብሔር፣ የቋንቋም ሆነ የሃይማኖት ልዩነት እንደ አካል አቅፋ በያዘችን ሀገር ውስጥ በሰላም ለመኖር የሚያስቸግረን አይደለም፡፡ ልዩነቶቻችን የሚጎዱን ወይም ጉዳት ያስከተሉብን ቢመስለን እንኳ እውነታው ግን ከዚህ የተለየ ሊሆን እንደሚችል ማሰብ መመርመርና በመከባበር መኖር ይገባናል፡፡ በመለያየት የምንጠቀም የሚመስለው ካለም ሐሳቡን እንደገና ቢያጤንና ቢመረምር ይሻላል እንላለን፡፡

2.የማኅበረሰብ መሪዎች የጭንቅላትን ሓላፊነት ቢወጡ መልካም ነው፡፡

በአሁኑ ወቅት በአንዳንድ አካባቢዎች እያጋጠሙ ያሉትን ችግሮች በአግባቡ ለመወጣትና በአካል ውስጥ እንዳሉ ብልቶች ተከባብሮ ለመኖር ማኅበረሰቡን የሚመሩ አካላት ሓላፊነትና ድርሻ ትልቅ መሆኑ የሚዘነጋ አይደለም፡፡ ስለዚህ መንግሥታዊ የሆኑም ሆነ መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት እና የማኅበረሰብ መሪዎች ሁሉ በዚህ ጊዜ እንደ ጭንቅላት ሆኖ ማኅበረሰቡን እንደ ብልት ማዋሐድና የሀገርንም ሆነ የሕዝብን ጤንነት ወዳልተፈለገ አቅጣጫ የሚወስዱ ግጭቶችን መፍታት ይጠበቅባቸዋል፡፡ የተለያዩ የሃይማኖት መሪዎች አማኞቻቸውን ሃይማኖት የታከከ ግጭት እንዳያስነሡና በዚህም ወዳልተፈለገ ሀገራዊ ቀውስ እንዳይገባ የመጠበቅ ሓላፊነት አለባቸው፡፡ ይህን ማድረግ እስካልተቻለ ድረስ ሁላችንም በተግባር ከመጎዳታችን በላይ በታሪክና በትውልድ ተጠያቂዎች እንሆናለን፤ መውጫውን በማናውቀው ገደልና የችግር አዙሪት (vicious circle) ውስጥም ስንዳንክር ልንኖር እንችላለን፡፡ ስለዚህም ነገሮቹን ሁሉ በአግባቡ የማየት ታሪካዊና ሰብአዊ ሓላፊነት እንዳለባቸው ተገንዝበው በፍጥነት የሚቻላቸውን ሁሉ ሊያደርጉ ይገባል፡፡ ሁላችንም ብንሆን ደግሞ በጠባብ ሐሳቦች፣ በቅርብ ጥቅሞችና ጠንካራና እውነት በሚመስሉ ነገር ግን ደካማና ስሕተት በሆኑ ትንታኔዎች ተይዘን እንዳንታለል ችግሮችንም እንዳናሰፋ ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡

3.ማኅበረሰባዊ መስተጋብሮችን ሊያናጉ የሚችሉ ልዩነቶችን ከማጉላት ችግሮችንም ከማስፋት መቆጠብ

እያንዳንዳችን እንደግለሰብም ሆነ እንደተቋም የምንኖርበት ዓለም ከሌሎቹ ጋር አንድ ስለሆነ ከግጭት፣ ከልዩነትና ከመሳሰሉት ነጻ የመሆን እድላችን በእጅጉ አነስተኛ ነው፡፡ ሆኖም ግለሰቦችም ሆኑ ተቋማት ችግሮችን የሚያዩበት፤ የሚተረጉሙበትና እርሱንም የሚያስረዱበትም ሆነ አቋም የሚይዙበት መንገድ ጉዳዩንና ችግሩን ወይ ይፈታዋል ካለበለዚያም ሊያባብሰው ይችላል፡፡ በአሁኑ ጊዜም ብዙ አካላትን የጥቃት ሰለባ እያደረጋቸውና ማኅበረሰባዊ ቀውሱንም እያባበሰው ያለው የችግሮች በሆነ አካባቢና ዓውድ መከሰታቸው ሳይሆን ከተጨባጭ እውነታው የራቀው መረዳታችን (Perception) እና አንዳንዴም አርቆ አሳቢና ተቆርቋሪነት ያለባቸው የሚመስሉ ትናታኔዎቻችንን መሠረት አድርገን በመጓዛችን ሊሆን ይችላል፡፡ ይህም ታሪክ ቀመስ ጉዳዮችን እየጠቀስን እርስ በርስ ከምንወራከብባቸው ብዙ ጉዳዮች መረዳት ይቻላል፡፡

ትላንት አሁን ያለው ትውልድ ባልነበረበት፣ እንዳሁኑ ዘመንም ሁሉም ነገር በመረጃ በማይታይበትና ባልተሰነደበት፣ አብዛኛዎቹም ነገሮች አሁን ያለው አካል ነቅፎም ሆነ ደግፎ በሚከራከርላቸው አቋሞች መሠረት ሆነ ተብለው የተደረጉ በማይመስሉ በዚያ ባለፈው ዘመን ክስተቶች ይህን ያክል ውርክብና እሰጥ አገባ ውስጥ ገብተን ከተቸገርን አሁን ራሳችንን አዋቂ አድርገንና ሆነ ብለን እወቁልኝና ስሙልኝ እያልን ብዙ ሚዲያዎችን ተጠቅመን በምናደርጋቸው ነገሮችማ ምን ያህል ችግሮችን ልንፈጥር እንደምንችል መገመት የሚያስቸግር አይመስለንም፡፡ ስለዚህም ምንም እንኳ ሰው ዓላማዬ ብሎ ለያዘው ነገር የሚችለውን ያህል መሥዋዕትነት እስከመክፈል መታገሉ የሚጠበቅ ቢሆንም ለማሸነፍ ወይም ተቆርቋሪና አለኝታ መስሎ ለመታየት በሚደረግ ሩጫ ግን ሳናውቀው ችግሮችን ከእውነታውና ከከባቢያዊ ዓውዳቸው አውጥተን ስሜታችንን በሌሎች ላይ በመጫን ልዩነትን እንዳናሠፋ ችግሮቻችንንም እንዳናውሰበስባቸው ስጋት አለን፡፡ ይህ ማለት አጥፊዎች አይጠየቁ ችግሮችም አይነሱ ማለት እንዳልሆነ ግልጽ ነው፡፡

አሁን የምናያቸው አብዛኞቹ ግጭቶች ግን ስለትላንት በምናወራው ላይ ሰሚዎቻችን ተናጋሪዎቹን አምነው የሚወስዷቸው አጸፌታዊ እርምጃዎች እንደሆኑ ይደመጣል፡፡ ስለዚህ ስላለፉትም ሆነ አሁን ስላሉት ነገሮች ስንነጋገርና ስንከራከር ዞሮ ዞሮ አንድነታችንን በሚያጠናክር ሓላፊነቱንና ተጠያቂነቱን ባልዘነጋ መልኩ ቢሆን መልካም ይሆናል፡፡ እውነታዎችን ሁሉ እርግጠኞች መሆን እስከምንችል ብናውቅ እንኳ በማወቃችን ብቻ አላስፈላጊ ነገሮችን ላለማድረግ ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ሁሉን ከመደረጉ በፊት የሚያውቀው ጌታችንም የይሁዳን የማታለልና የማሳመጽ ተግባር ለሚወዱትና ለሚከተሉት ሐዋርያት እንኳ ቶሎ አልገለጸላቸውም፡፡ በዚህም እውነቱን በማወቃችን ብቻ የአንድን ነገር ውጤት ሳናስብና ጉዳቱን ሳንመረምር አፋችን እንዳመጣ ያለጊዜው እንዳንናገር አስተማረን፡፡ ስለዚህም በቤተ ክርስቲያንም ሆነ በሀገር ደረጃ የምናያቸው ችግሮች ከተፈጠሩ በኋላ ስሜታዊ መሆን አያስፈልገንም፡፡ ይልቁንም ደጋግመን እንደገለጽነው መኖራቸውን ተቀብለን መፈጠራቸውንም እውቅና ሰጥተን ከስሜትና ከችኮላ ተላቅቀን የራሳችንን ትርጉምና መረዳት ብቻ እንደ እውነት ቆጥረን ከመንቀሳቀስ መቆጠብ፣ ካለፈው የተሻልን ሆነን፣ ችግሮቹን ከማስፋት ወደ ማጥበብ መጓዝ ይኖርብናል፡፡ ይህንንም ለማድረግ ጉዳዮችን በጥልቀት መመርመርና ማጥናት በመፍትሔዎቹም ላይ በመደማመጥ መወያየት ያስፈልጋል፡፡

4.በራሳችን የሓላፊነት ስፍራ ውስጥ ብቻ ሥራችንን መሥራት

በአሁኑ ወቅት ችግሮቻችንን እያሰፉና በየአቅጣጫው የሴራ ትንታኔዎች ገዝፈው ሰዎችን በመረዳታቸው መጠን የራሳቸውን እርምጃ በመውሰድ ችግር ውስጥ እንዲገቡ ከሚገፉ ነገሮች፣ ዋነኛው ግለሰቦችም ሆኑ ተቋማት የእነርሱ ባልሆነ ቦታ ውስጥ የሚፈጽሙት ደባና ተንኮል ይመስለናል፡፡ ምንም እንኳ በፖለቲካዊ ዓለም ይህ አሠራር ራሱን የቻለ ሳይንሳዊ ዘዴ ያለው ስልት ቢሆንም በተለይ በእምነት ተቋማት ግን አደገኛና ትልቅ ችግር አምጭ መሆኑን ለመረዳት የሚያስቸግር አይመስልም፡፡ ለዚህም እንደ ምሳሌ ራሳቸውን “ተሐድሶ ዘኦርቶዶክስ” ብለው የሚጠሩ አካላት እየፈጠሩ ያሉትን ችግር ሁሉም አካል በአግባቡ እንዲገነዘበው መሪዎቻቸውም ይህንኑ ሓላፊነት በአግባቡ እንዲወጡ ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡

ራስን ችሎ በሚያምኑበት ሃይማኖት መመራትና ማምለክ እየተቻለ፤ በነባሯና በጥንታዊዋ ሃይማኖት ውስጥ ሠርጎ በመግባትና እራስን ደብቆ ችግሮችን በማባባስ የፈለጉት ቦታ ለመድረስ የሚቻል ቢመስልም፤ እውነታው ከዚህ ሩቅ መሆኑን ተገንዝቦ መሔድ ወቅቱ የሚፈልገው መፍትሔ ነው፡፡ ለራስ የተለየ ግምት በመስጠት ሁሉን ማድረግ እንደሚቻል በማሰብ የተለያዩ የተንኮልና የማስመሰል ዘዴዎችን ተጠቅሞ ችግር ለመፍጠር መሞከር እውነታውን አይለውጥም፡፡ ለአንዳንድ ሞኞችም ተንኮል ጥበብ፣ እብሪትም አሸናፊነት ቢመስላቸውም እውነታው ሁልጊዜም የተለየ ነው፡፡ መፍቀሬ ጥበብ ሰሎሞን ታካች ሰው በጥበብ ከሚመልሱ ከሰባት ሰዎች ይልቅ ለራሱ ጠቢብ የሆነ ይመስለዋል /ምሳ 26፥16/ እንዳለው የተጠበብንና የተራቀቅን ቢመስለንም ሞኝነታችን የተገለጠ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ የጥበበኞችን ጥበብ አጠፋለሁ የአስተዋዮችንም ማስተዋል እጥላለሁ ተብሎ ተጽፎአልና። ጥበበኛ የት አለ? ጻፊስ የት አለ? የዚች ዓለም መርማሪስ የት አለ? እግዚአብሔር የዚችን ዓለም ጥበብ ሞኝነት እንዲሆን አላደረገምን? /1ኛ ቆሮ 1 ፥ 19 – 21/ እንዳለው በከንቱ ከመድከም ያመኑበትን በይፋ ይዞ በራስ ቦታ ተወስኖ በመሔድ በግልጽ የማስተማርም ሆነ የማምለክ ነጻነቱ ስላለ ይህንን ሓላፊነት መወጣት አማራጭ የሌለው መፍትሔ መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ሽንገላዎች፣ ጥበብና ቻይነት የሚመስሉ ተንኮሎች፣ ችግሮችን አውሰብስበው ራስን ከመጉዳት በቀር የሚያመጡት ጠቀሜታ አይኖርም፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን በሓላፊነት ያሉ አካላትም የታመመውን ብልት እያከሙ እያዳኑ የአካልን ጤንነት መጠበቅ ግዴታቸው መሆኑን እንደማይዘነጉት እሙን ነው፡፡ ሆኖም አንዳንዱ በሽታ የበከለው ብልት በሕክምና የማይድንና ሌላውንም ቀስ በቀስ እያጠቃ አካልን የሚጎዳው፣ መላ ሰውነትንም የሚያጠፋ ከሆነ ደግሞ፣ እርሱን እንደ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በጊዜው ቆርጦ ሌላውን አካል ማዳን አሁንም ጭንቅላት ከተሰኙ የቤተ ክርስቲያኒቱ የተለያዩ ሓላፊዎች የሚጠበቅ ተግባር መሆኑ መረሳት የለበትም፡፡ ካለበለዚያ ጭንቅላትን ጨምሮ መላውን አካል ማወኩ ማስጨነቁና ብሎም ለሞት መዳረጉ አይቀርምና ሓላፊነትን በአግባቡና በጊዜው መወጣት ይጠይቃል እንላለን፡፡

በአጠቃላይ በአሁኑ ወቅት ያሉብንን ችግሮች በሰከነ መንገድ በአግባቡ መፍታት ከሁላችንም የሚጠበቅ ተግባር ሆኖ ይታየናል፡፡ ልዩ ልዩ መንግሥታዊ አካላት፤ ልዩ ልዩ የማኅብረሰብ መሪዎች ሁሉ በሰከነ መንገድ የጭንቅላትነት ማለትም የማሰብ ሁሉንም ብልት የመጠበቅ የመንከባከብና የአካል መለያየት እንዳይኖር ነቅቶ የመጠበቅ ታሪካዊ ሓላፊነታቸውን መወጣት ይጠበቅባቸዋል የሚል እምነት አለን፡፡ በተለይም ልዩነቶቻችን እንደ ሰውነት ብልቶች ከመጠቃቀሚያነት ወደ መደባደቢያነትና ጎሳን ብሔርን ቋንቋንና ሃይማኖትን መሠረት አድርጎ ግጭት ውስጥ እንዳይገባ ሓላፊነትን በአግባቡ መወጣት የሁሉም ድርሻ ሊሆን ይገባል፡፡ ካለበለዚያ አንድ ብልት ያመጣው በሽታ መላው አካልን እንደሚጎዳው ሰውነትንም እንደሚያጠፋው ጥፋቱ ለሚመሩት አካል ጭንቅላት ለሆኑትም እንደማይቀር አስበን ካልሠራን ጉዳቱ አይቀርልንም፤ ከእውነታው ጋርም እንደተጣላን እንቀራለን፡፡ ስለዚህ አስቀድመን ከሚመስለንና ከግምታችን ወጥተን እውነቱን እንያዝ ከሚሆነውም አንቃረን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡