ፅንሰተ ድንግል ወተስእሎተ ቂሣርያ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በነሐሴ ወር በሰባተኛው ቀን ከሚከብሩ በዓላት መካከል በዛሬው ዝግጅታችን የእመቤታችንን ፅንሰት እና ተስእሎተ ቂሣርያን የተመለከተ ጽሑፍ ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡ በመጀመሪያም ፅንሰተ ድንግል ማርያምን እናስቀድም፤

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን ለማዳን ሲል በዕለተ ዓርብ በመስቀል ላይ የቈረሰውና ያፈሰሰው፤ እርሱን የበሉና የጠጡ ኹሉ መንግሥቱን የሚወርሱበት፤ ዘወትር በቤተ መቅደሱ የሚፈተተው ቅዱስ ሥጋውና የሚቀዳው ክቡር ደሙ ከንጽሕተ ንጹሐን፣ ከቅድስተ ቅዱሳን ከወላዲተ አምላክ ድንግል ማርያም የተዋሐደው ሥጋና ደም ነው፡፡ እመቤታችንን እናታችን፣ አማላጃችን፣ የድኅነታችን ምክንያት፣ ወዘተ እያልን የምናከብራት፣ የምናገናት፣ የምንወዳት ዘለዓለማዊ ሕይወት የሚሰጠውን፤ ከሞተ ሥጋ ከሞተ ነፍስ ማዳን የሚቻለውን፤ እውነተኛውን ምግበ ሥጋ ወነፍስ ኢየሱስ ክርስቶስን ስለወለደችልን ነው፡፡ ‹‹ኦ ማርያም በእንተዝ ናፈቅረኪ ወናዓብየኪ እስመ ወለድኪ ለነ መብልዐ ጽድቅ ዘበአማን ወስቴ ሕይወት ዘበአማን፤ ማርያም ሆይ እውነተኛውን ምግብ፣ እውነተኛውን መጠጥ አስገኝተሽልናልና እናከብርሻለን፤ እናገንሻለን፤›› እንዳለ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴ ማርያም፡፡

ቅዱስ ዳዊት ‹‹ቀደሰ ማኅደሮ ልዑል …፤ ልዑል እግዚአብሔር ማደሪያውን መረጠ፤ አከበረ፤ ለየ፤ ቀደሰ …›› /መዝ.፵፭፥፬/ በማለት እንደተናገረው አምላክን በማኅፀኗ ለመሸከም የተመረጠችው ማኅደረ ማለኮት ቅድስት ድንግል ማርያም የተፀነሰችው ነሐሴ ፯ ቀን ነው፡፡ ፅንሰቷም እግዚአብሔር በባረከውና ባከበረው ቅዱስ ጋብቻ በተወሰኑት ወላጆቿ በቅዱስ ኢያቄምና በቅድስት ሐና ሥርዓት ያለው ግንኙነት አማካይነት ነው፡፡ ‹‹ኦ ድንግል አኮ በፍትወተ ደነስ ዘተፀነስኪ አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ፤ ድንግል ሆይ በሥጋዊ ፈቃድ የተፀንሽ አይደለሽም፤ ሕጋዊ በኾነ ሥርዓት ከሐና እና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጂ›› እንዲል /ቅዳሴ ማርያም/፡፡

ታሪኩን ለማስታዎስ ያህልም የእመቤታችን ቅድመ አያቶቿ ቴክታ እና በጥሪቃ ይህ ቀራቸው የማይባሉ ባለጠጎች እና መካኖች ነበሩ፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን በጥሪቃ ከቤተ መዛግብት ገብቶ የገንዘባቸውንና የንብረታቸውን ብዛት አይቶ ሚስቱ ቴክታን ‹‹አንቺ መካን፤ እኔ መካን፡፡ ይህ ኹሉ ገንዘብ ለማን ይኾናል?›› አላት፡፡ ቴክታም ‹‹እግዚአብሔር ከእኔ ልጅ ባይሰጥህ ከሌላ ይሰጥህ ይኾናል፡፡ ሌላ ሚስት አግብተህ ልጅ አትወልድምን?›› ባለችው ጊዜ ‹‹ይህንስ እንዳላደርገው አምላከ እስራኤል ያውቃል›› አላት፡፡ በዚህ ጊዜ ኹለቱም እያዘኑ ሳሉ ነጭ እንቦሳ (ጥጃ) ከበረታቸው ስትወጣ፤ እንቦሳይቱ እንቦሳ እየወለደች እስከ ስድስት ልጅ ስትደርስና ስድስተኛዪቱ እንቦሳም ጨረቃን፣ ጨረቃም ፀሐይን ስትወልድ ራእይ አዩ፡፡

ራእያቸውን ለሕልም ተርጓሚ ሲነግሩም ‹‹የጨረቃዪቱ ትርጕም ከፍጡራን በላይ የምትኾን ልጅ እንደምታገኙ የሚያመለክት ነው፡፡ የፀሐይ ነገር ግን አልተገለጠልኝም፡፡ እንደ ነቢይ፣ እንደ ንጉሥ ያለ ይኾናል፤›› አላቸው፡፡ እነርሱም ‹‹ጊዜ ይተርጕመው ብለው›› ወደ ቤታቸው ከተመለሱ በኋላ ቴክታ ፀንሳ ሴት ልጅ ወለደች፤ ስሟንም ሄኤሜን አለቻት፡፡ ትርጕሙም ስእለቴን (ምኞቴን) አገኘሁ ማለት ነው፡፡ ሄኤሜን ዴርዴን፤ ዴርዴ ቶናን፤ ቶና ሲካርን፤ ሲካር ሄርሜላን፤ ሄርሜላ ሐናን ወለደች፡፡ ሐና ለዓቅመ ሄዋን ስትደርስም ኢያቄም ለሚባል ደግ ሰው አጋቧት፡፡ እነርሱም እንደ በጥሪቃና ቴክታ መካኖች ነበሩ፡፡ በእስራኤላውያን ባህል መካንነት የእርግማን ምልክት ተደርጎ ይቈጠር ነበርና ሐና እና ኢያቄም ብዙ ዘለፋና ሽሙጥ ይደርስባቸው ነበር፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን መሥዋዕት ለማቅረብ ወደ ቤተ መቅደስ ቢሔዱ የዘመኑ ሊቀ ካህናት ሮቤል መካን መኾናቸውን ያውቅ ነበርና ‹‹እናንተማ ‹ብዙ ተባዙ› ብሎ እግዚአብሔር ለአዳም የነገረውን ያስቀረባችሁ ርጉማን አይደላችሁምን? እግዚአብሔር ቢጠላችሁ እንጂ ቢወዳችሁማ ልጅ ይሰጣችሁ አልነበረምን?›› ብሎ መሥዋዕታቸውን ሳይቀበላቸው በመቅረቱ፤ አንድም ከአዕሩገ እስራኤል (ከአረጋውያን እስራኤላውያን) የተወለዱ ሰዎች የሚመገቡትን ተረፈ መሥዋዕት እንዳይመገቡ በመከልከሉ እያዘኑ ሲመለሱ ከልጆቻቸው ጋር የሚጫወቱ ርግቦችንና አብበው ያፈሩ ዕፀዋትን ሐና በተመለከተች ጊዜ ‹‹ርግቦችን በባሕርያቸው መራባት እንዲችሉ፤ ዕፀዋትን አብበው እንዲያፈሩ የምታደርግ ጌታ እኔን ለምን ልጅ ነሳኸኝ?›› ብላ አዘነች፡፡

ከቤታቸው ሲደርሱም ‹‹እግዚአብሔር ልጅ ቢሰጠን ወንድ ከኾነ ለቤተ እግዚአብሔር ምንጣፍ አንጣፊ፣ መጋረጃ ጋራጅ ኾኖ ሲያገለግል ይኑር፤ ሴት ብትኾንም መሶበ ወርቅ ሰፍታ፣ መጋረጃ ፈትላ ስታገለግል ትኑር›› ብለው ከተሳሉ በኋላ ሐምሌ ፴ ቀን ሐና ለኢያቄም ‹‹በሕልሜ ፀምር (መጋረጃ) ሲያስታጥቁህ፤ በትርህ አፍርታ ፍጥረት ኹሉ ሲመገባት አየሁ›› ብላ ያየቸውን ራእይ ነገረችው፡፡ ኢያቄም ደግሞ ለሐና ‹‹ጸዓዳ ረግብ ሰባቱን ሰማያት ሰንጥቃ መጥታ በራስሽ ላይ ስታርፍ፣ በቀኝ ጆሮሽ ገብታ በማኅፀንሽ ስታድር አየሁ›› ብሎ ያየውን ራእይ ነገራት፡፡ ሕልም ተርጓሚው ‹‹ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ›› ባላቸው ጊዜም ‹‹አንተ አልፈታኸውም፤ ጊዜ ይፍታው›› ብለው ተመልሰዋል፡፡

ከዚህ በኋላ የእግዚአብሔር መልአክ መጥቶ ‹‹ደግ ልጅ ትወልዳላችሁ›› ብሎ ነግሯቸው ሐዲስ ኪዳን ሊበሠር፤ ጌታችን ሊፀነስ ፲፬ ያህል ዓመታት ሲቀሩ ነሐሴ ፯ ቀን በፈቃደ እግዚአብሔር እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተፀንሳለች፡፡ እመቤታችን በሐና ማኅፀን ውስጥ ሳለች ከተደረጉ ተአምራት መካከልም በርሴባ የምትባል አንድ ዓይና ሴት (አክስቷ) ሐናን ‹‹እግዚአብሔር በረድኤት ጐበኘሽ መሰለኝ ጡቶችሽ ጠቁረዋል፤ ከንፈሮችሽ አረዋል›› ብላ ማኅፀኗን በዳሰሰችበት እጇ ብታሸው ዓይኗ በርቶላታል፡፡ ይህንን አብነት አድርገውም ብዙ ሕሙማን ከደዌያቸው ተፈውሰዋል፡፡ ዳግመኛም ሳምናስ የሚባል ያጎቷ ልጅ በሞተ ጊዜ ሐና የአልጋውን ሸንኮር ይዛ ስታለቅስ ጥላዋ ቢያርፍበት ከሞት ተነሥቶ ‹‹ሰላም ለኪ ኦ እምሔውቱ ለዘገብረ ሰማየ ወምድረ፤ ሰማይና ምድርን የፈጠረው አምላክ አያቱ ሐና ሆይ ሰላም ላንቺ ይኹን›› ብሎ ሕልም ተርጓሚው ያልፈታውን ራእይ በመተርጐም ከሐና እመቤታችን፤ ከእመቤታችን ደግሞ እውነተኛ ፀሐይ የተባለው ክርስቶስ እንሚወለድ አስቀድሞ ተናግሯል፡፡ /ምንጭ፡- ቅዳሴ ማርያም አንድምታ ትርጓሜ፣ ፭፥፴፰/፡፡

በየዓመቱ ነሐሴ ፯ ቀን የሚዘከረው ሌላኛው በዓል ደግሞ ‹‹ተስእሎተ ቂሣርያ›› የሚባለው የጌታችን በዓል ነው፤ የቃሉ (ሐረጉ) ትርጕም በቂሣርያ አገር የቀረበ ጥያቄ ማለት ሲኾን ይኸውም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ሰዎች ማን ይሉኛል?›› ብሎ ደቀ መዛሙርቱን መጠየቁን ያስረዳል፡፡ በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈ ጌታችን በቂሣርያ አውራጃ ሐዋርያቱን ሰብስቦ ‹‹ሰዎች የሰውን ልጅ (ኢየሱስ ክርስቶስን) ማን ይሉታል?›› ብሎ ሲጠይቃቸው እነርሱም ‹‹ዮሐንስ፣ ኤልያስ፣ ኤርምያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው ይላሉ›› የሚል ምላሽ ሰጥተውታል፡፡ እርሱም መልሶ ‹‹እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ?›› የሚል ጥያቄ ባቀረበላቸው ጊዜ የሐዋርያት አለቃ ቅዱስ ጴጥሮስ ሐዋርያቱን ወክሎ ‹‹አንተ ውእቱ ክርስቶስ ወልደ እግዚአብሔር ሕያው፤ አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ›› ብሎ የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት የሚያስረዳ ምላሽ ሰጥቷል፡፡

የቅዱስ ጴጥሮስ ምላሽም ሰዎች ስለ ክርስቶስ ማንነት ከሚሰጡት ግምትና ከሐዋርያት ዕውቀት በላይ በመኾኑ ጌታችን ‹‹የእኔን አምላክነት ሰማያዊ አባቴ ገለጸልህ እንጂ ሥጋዊ ደማዊ አእምሮ አልገለጸልህም›› በማለት አድንቆለታል፡፡ ከዚህ በኋላ ‹‹አንተ አለት ነህ፤ በአንተ መሠረትነት ቤተ ክርስቲያኔን እሠራታለሁ፡፡ የገሃነም ደጆች (አጋንንት) አይችሏትም፡፡ የመንግሥተ ሰማያትን መክፈቻ እሰጥሃለሁ፡፡ በምድር ያሠርኸው በሰማይም የታሠረ፤ በምድር የፈታኸው በሰማይም የተፈታ ይኾናል›› በማለት ለስብከተ ወንጌል መስፋፋት፣ ለቤተ ክርስቲያናችን መታነፅ፣ ለምእመናን ድኅነት ምክንያት የኾነውን መዓርገ ክህነት ሰጥቶታል /ማቴ.፲፮፥፲፫-፲፱/፡፡

ይህም ሥልጣነ ክህነት በቅዱስ ጴጥሮስ አንጻር ከሐዋርያት ጀምሮ ለሚነሡ አባቶች ካህናት የተሰጠ ሰማያዊ ሀብት ነው፡፡ ዛሬ ምእመናን በኀጢአት ስንሰናከል ከካህናት ፊት ቀርበን የምንናዘዘውና ንስሐ የምንቀበለው፣ እንደዚሁም እየተባረክን ‹‹ይፍቱኝ›› የምንለው ጌታችን ለእነርሱ የሰጣቸውን ሥልጣነ ክህነት መሠረት በማድረግ ነው፡፡ ካህናትም ‹‹ይኅድግ ይፍታሕ ያንጽሕ ወይቀድስ …›› እያሉ ከናዘዙን በኋላ ‹‹እግዚአብሔር ይፍታ›› የሚሉን ከባለቤቱ የማሠር የመፍታት ሥልጣን ስለ ተሰጣቸው ነው፡፡

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰዎች ስለ እርሱ የሚናገሩትንም፣ የሚያስቡትንም የሚያውቅ አምላክ ሲኾን በቂሣርያ ሐዋርያቱን ‹‹ሰዎች ማን ይሉኛል›› ብሎ መጠየቁ በአንድ በኩል አላዋቂ ሥጋን መልበሱን ለማጠየቅ፤ በሌላ ምሥጢር ደግሞ ሐዋርያቱን ‹‹እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ›› ብሎ በመጠየቅ አምላክ ወልደ አምላክ መኾኑን ለመግለጥና መዓርገ ክህነትን ለሐዋርያትና ለተከታዮቻቸው (ለጳጳሳት፣ ቀሳውስትና ዲያቆናት) ለመስጠት ነው፡፡ ይህም በቅዱስ ጴጥሮስ ምላሽና ጌታችን ለጴጥሮስ በሰጠው ሥልጣን ይታወቃል፡፡

በዚህ በተስእሎተ ቂሣርያ ጌታችን ሐዋርያቱ ማን እንደሚሉት ስለ ማንነቱ ከጠየቃቸው በኋላ ምላሻቸውን ተከትሎ ሥልጣነ ክህነትን መስጠቱም በብሉይ ኪዳን (እግዚአብሔር በሥጋ ከመገለጡ በፊት) አዳም የት እንዳለ እያወቀ ‹‹አዳም ሆይ ወዴት ነህ?›› /ዘፍ.፫፥፲/ ብሎ ከጠየቀውና ያለበትን እንዲናገር ካደረገው በኋላ ‹‹ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ›› የሚል የድኅንት ቃል ኪዳን መግባቱን ያስታውሰናል /ቀሌምንጦስ/፡፡ እንደዚሁም እግዚአብሔር በሦስትነቱ ከአብርሃም ቤት በገባ ጊዜ ሣራ ያለችበትን ቦታ እያወቀ አብርሃምን ‹‹ሚስትህ ሣራ ወዴት ናት?›› ሲል ያለችበትን ቦታ ካናገረው በኋላ ‹‹ሣራ የዛሬ ዓመት ልጅን ታገኛለች›› የሚል በአንድ በኩል የይስሐቅን መወለድ፤ በሌላ በኩል ደግሞ የእግዚአብሔርን ሰው መኾንና የሐዲስ ኪዳንን መመሥረት የሚያበሥር ቃል መናገሩ ከዚህ ትምህርት ጋር ተመሳሳይነት አለው /ዘፍ.፲፰፥፱-፲፭/፡፡

በሐዲስ ኪዳንም አልዓዛር በሞተ ጊዜ የተቀበረበትን ቦታ እያወቀ ‹‹አልዓዛርን ወዴት ቀበራችሁት›› /ዮሐ.፲፩፥፴፯/ ብሎ መካነ መቃብሩን ከጠየቀ በኋላ በሥልጣኑ ከሞት እንዲነሣ ማድረጉም ከተስእሎተ ቂሣርያ ጋርና ከላይ ከጠቀስናቸው ምሳሌዎች ጋር የሚወራረስ ምሥጢር አለው፡፡ ይኼ ኹሉ ቃል እግዚአብሔር ያላወቀ መስሎ በመጠየቅ የሰዎችን ስሜት እንደሚገልጥና የልባቸውን መሻትና እምነት መሠረት አድርጎ ሥልጣንን፣ በረከትንና ጸጋን እንደሚያድል የሚያስረዳ ትምህርት ነው፡፡ ለዚህም ጌታችን በመዋዕለ ሥጋዌው በምድር በአካለ ሥጋ ሲመላለስ መዳን እንደሚፈልጉ እያወቀ ‹‹ልትድን ትወዳለህን? (ልትድኚ ትወጃለሽን?) እያለ በመጠየቅ የልባቸውን መሻት እንዲናገሩ ካደረገ በኋላ እምነታቸውን አይቶ ‹‹ፈቀድኩ ንጻሕ /ንጽሒ፤ ፈቅጃለሁ ተፈወስ /ተፈወሺ›› እያለ በአምላካዊ ቃሉ ለሕሙማነ ሥጋ ወነፍስ ፈውስን ማደሉ ትልቅ ማስረጃ ነው፡፡

በአጠቃላይ ‹‹እመቤታችን ከእርሷ እንድትወለድ ዐውቆ አዳም ሔዋንን ሕይወቴ ነሽ ይላት ነበር›› እንደ ተባለው የኹላችንም ሕይወት፤ የዓለሙን ቤዛ በመውለዷ ቤዛዊተ ዓለም እየተባለች የምትጠራው፤ በአምላክ ሕሊና ታስባ ትኖር የነበረችው የድኅነታችን ምክንያት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በማኅፀን የተቋጠረችው፤ ዳግመኛም በቂሣርያ ሐዋርያት ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት የመሰከሩት፣ እርሱም ሥልጣነ ክህነትን የሰጣቸው በዚህች ዕለት ነውና በመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በየዓመቱ ነሐሴ ፯ ቀን በድምቀት ይከበራል፡፡ እናቱን በአማላጅነት፤ ራሱን በቤዛነት ለሰጠን ለልዑል እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይድረሰው፤ የእመቤታችን በረከት አይለየን፡፡

ጾመ ፍልሰታ ለማርያም

 ነሐሴ ፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው  

በነገረ ማርያም ተጽፎ እንደምናገኘው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጥር ፳፩ ቀን በ፵፱ ዓ.ም ከዚህ ዓለም ድካም ባረፈች ጊዜ ቅዱሳን ሐዋርያት ሊቀብሯት ወደ ጌቴሴማኒ ይዘዋት ሲሔዱ አይሁድ “እንደ ልጇ ተነሣች፤ ዐረገች እያሉ እንዳያውኩን በእሳት እናቃጥላት” ብለው በዓመፃ ተነሡ፡፡ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊም አጎበሩን ይዞ ሊያወርዳት ሲል የእግዚአብሔር መልአክ ሁለት እጆቹን ቀጥቶታል፡፡ ከዚህ በኋላ እግዚአብሔር አምላክ ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስን ጨምሮ እመቤታችንን በደመና ነጥቆ ወደ ገነት ወስዶ ከዕፀ ሕይወት ሥር አስቀመጣት፡፡

 

ቅዱሳን ሐዋርያትም እመቤታችን ያለችበት ቦታ እንዲገለጥላቸው ባረፈች በስምንተኛው ወር ከነሐሴ ፩ ቀን ጀምረው ሱባዔ ገብተው እግዚአብሔርን በጸሎት መጠየቅ ጀመሩ፡፡ ከዚህ ላይ “ስምንት ወር ሙሉ ምን ይዘው ቆይተው ነሐሴ ላይ ሱባዔ ገቡ?” የሚል ጥያቄ ሊነሣ ይችላል፡፡ በእውነቱ ቅዱሳን ሐዋርያት ከስብከተ ወንጌል፣ ከጾም፣ ከጸሎት፣ ከገቢረ ተአምራት፣ ተለይተው እንደማያውቁ መንፈሳዊ ሕይወታቸው ምስክር ነው፡፡

 

በመኾኑም እመቤታችን ካረፈችበት ቀን ከጥር ወር ጀምሮ እስከ ነሐሴ ድረስ ጥያቄያቸውንና ጸሎታቸውን ባያቋርጡም ከሰው ተለይተው ሱባዔ ገብተው ጾም ጸሎት የጀመሩት ግን ከነሐሴ ፩ ቀን ጀምረው ነው፡፡ ቀድሞስ የክብር ባለቤት የጌታችን የመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርት ኾነው እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም ተሠውራባቸው እንዴት ዝም ብለው ይቀመጣሉ?

 

ሁለት ሱባዔ ካደረሱ በኋላም የነገሩትን የማይረሳ፣ የለመኑትን የማይነሳ እግዚአብሔር አምላካችን ጸሎታቸውን ሰምቶ ነሐሴ ፲፭ ቀን የእመቤታችንን ሥጋ ሰጥቷቸው በክብር ገንዘው በጌቴሴማኒ ቀብረዋታል፡፡ በሦስተኛው ቀንም እንደ ልጇ እንደ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይታ ተነሥታለች፡፡ “ከመ ትንሣኤ ወልዳ፤ እንደ ልጇ ትንሣኤ” ያሰኘውም ይህ ታሪክ ነው፡፡

 

ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ሲሰብክ ቆይቶ ደመና ጠቅሶ ከሀገረ ስብከቱ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመጣ እመቤታችን ከሙታን ተለይታ ተነሥታ ወደ ሰማይ ስታርግ አገኛት፡፡ በዚህ ጊዜ “ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ፤ ዛሬ ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁን?” ብሎ ትንሣኤዋን ባለማየቱ ኀዘን ስለ ተሰማው ከደመናው ይወድቅ ዘንድ ወደደ፡፡ “ወፈቀደ ይደቅ እምደመናሁ” እንዲል፡፡ እመቤታችንም “አይዞህ አትዘን፤ ባልነጀሮችህ ሐዋርያት ያላዩትን ትንሣኤዬን አንተ አይተሃል” ብላ ከሙታን ተለይታ መነሣቷንና ማረጓን እንዲነግራቸው አዝዛ የያዘቸውን ሰበን ሰጥታ ሰደደችው፡፡

 

እርሱም ትእዛዟን ተቀብሎ በክብር ከተሰናበታት በኋላ ወደ ሐዋርያት ሔዶ እንዳልሰማ እንዳላየ መስሎ “የእመቤታችን ነገር እንደምን ኾነ?” አላቸው፡፡ እነርሱም “አግኝተን ቀበርናት” ሲሉት “ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር እንዴት ይኾናል?” አላቸው፡፡  በዚህ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ከዚህ በፊት የክርስቶስን ትንሣኤ መጠራጠሩን ጠቅሶ እየገሠፀ ስለ እመቤታችን መቀበር እነርሱ የሚነግሩትን ኹሉ መቀበል እንደሚገባው ለቅዱስ ቶማስ አስረዳው፡፡ ቅዱስ ቶማስም የያዘውን ያውቃልና ጸጥ ብሎ ሲሰማው ቆየ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ተቈጥቶ የእመቤታችንን ክቡር ሥጋ ለቅዱስ ቶማስ ለማሳየት ሔዶ መቃብሯን ቢከፍት የእመቤታችንን ሥጋ ሊያገኘው አልቻለም፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ደንግጦ ቆመ፡፡

 

ቅዱስ ቶማስም “አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ከሙታን ተለይታ ተነሥታ ስታርግ አግኝቻታለሁ” ብሎ የሰጠችውን ሰበን ለሐዋርያት ሰጥቷቸዋል፡፡ እነርሱም በእመቤታችን ትንሣኤና ዕርገት እየተደሰቱ ሰበኑን ለበረከት ተካፍለውታል፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንደሚያስተምሩን በቅዳሴ ጊዜ ሠራዒ ዲያቆኑ በሚይዘው መስቀል ላይ የሚታሠረው መቀነት መሰል ልብስ፤ እንደዚሁም አባቶች ካህናት በመስቀላቸው ላይ የሚያደርጉት ቀጭን ልብስና በራሳቸው የሚጠመጥሙት ነጭ ሻሽ የእመቤታችን ሰበን ምሳሌ ነው፡፡

 

በዓመቱ ቅዱሳን ሐዋርያት “ቶማስ የእመቤታችን ትንሣኤዋንና ዕርገቷን አይቶ እኛ እንዴት ሳናይ እንቀራለን?” ብለው ከየሀገረ ስብከታቸው ተሰባስበው ጌታችን ሥጋዋን እንዲሰጣቸው በጠየቁበት በዚሁ ወቅት ከነሐሴ ፩ ቀን ጀምረው ሱባዔ ቢይዙ ጌታችን ልመናቸውን ተቀብሎ ነሐሴ ፲፮ ቀን እመቤታችንን መንበር፤ ጴጥሮስን ተራዳኢ ካህን፤ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ እመቤታችንንም ሐዋርያትንም አቍርቧቸዋል፡፡ እነርሱም እመቤታችንን በዓይናቸው ከማየት ባሻገር አብረው ሥጋውን ደሙን ተቀብለዋል /ትርጓሜ ውዳሴ ማርያም/፡፡

 

ይህንን ትምህርት መሠረት በማድረግ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ከነሐሴ ፩-፲፭ ያለው ሁለት ሱባዔ ከሰባቱ አጽዋማት አንዱ ኾኖ በምእመናን ዘንድ መጾም እንደሚገባው ሥርዓት ሠርተውልናል /ፍት.ነገ.አን.፲፭/፡፡ ይህ ጾምም “ጾመ ማርያም (የማርያም ጾም)” ወይም “ጾመ ፍልሰታ ለማርያም (የማርያም የፍልሰቷ ጾም)” እየተባለ ይጠራል፡፡ ‹ፍልሰት› የሚለው ቃልም “ፈለሰ ሔደ፤ ተሰደደ” ካለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲኾን ትርጕሙም ከአንድ አገር ወደ ሌላ አገር መሔድን ያመለክታል፡፡ ‹ፍልሰታ ለማርያም› ሲልም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ካረፈች በኋላ ከጌቴሴማኒ ወደ ገነት መወሰዷን የሚያስረዳ መልእክት አለው፡፡

 

በጾመ ፍልሰታ በቤተ ክርስቲያናችን በየቀኑ በማኅሌቱ፣ በሰዓታቱና በቅዳሴው በሚደርሰው ቃለ እግዚአብሔር ነገረ ማርያም ማለትም የእመቤታችን ከመፀነሷ ጀምሮ እስከ ዕርገቷ ድረስ ያለው ታሪኳ፣ ለአምላክ ማደሪያነት መመረጧ፣ ንጽሕናዋ፣ ቅድስናዋ፣ ክብሯ፣ ርኅርራኄዋ፣ ደግነቷ፣ አማላጅነቷ፣ ሰውን ወዳድነቷ በስፋት ይነገራል፡፡ እመቤታችንን ከሚያወድሱ ድርሳናት መካከልም በተለይ ምሥጢረ ሥላሴን፣ ምሥጢረ ሥጋዌንና ነገረ ድኅነትን ከነገረ ማርያም ጋር በማዛመድ የሚያትተው ቅዳሴ ማርያም፤ እንደዚሁም ነገረ ድኅነትን ከምሥጢረ ሥጋዌ (ከነገረ ክርስቶስ) እና ከነገረ ማርያም ጋር በማመሣጠር የሚያትተው ውዳሴ ማርያምም በስፋት ይጸለያል፤ ይቀደሳል፤ ይተረጐማል፡፡ በሰንበታት የሚዘመሩ መዝሙራት፤ በየዕለቱ በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለተዋሕዶ በእግዚአብሔር መመረጧን፣ ዘለዓለማዊ ድንግልናዋን፣ ክብሯን፣ ቅድስናዋን፣ ንጽሕናዋን የሚያወሱ ናቸው፡፡

 

በጾመ ፍልሰታ ባሕታውያን ብቻ ሳይኾኑ ዓለማውያንም በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በእመቤታችን አማላጅነት የሰይጣንን ፈተና ድል ለማድረግ እንዲቻላቸው ከቤተሰቦቻቸው ተለይተው በየገዳማቱና በየአብያተ ክርስቲያናቱ በዓት አዘጋጅተው፣ ሱባዔ ገብተው፣ ፈቃደ ሥጋቸውን ለፈቃደ ነፍሳቸው አስገዝተው ይጾማሉ፤ ይጸልያሉ፡፡ እንደዚሁም ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ይቀበላሉ፡፡ እኛም የእመቤታችንን ዕረፍትና ትንሣኤ በማሰብ ከልጇ ከወዳጇ የሚገኘውን ጸጋና በረከት ተስፋ በማድረግ የአባቶቻችንንና የእናቶቻችንን ፈለግ ተከትለን በየዓመቱ ጾመ ፍልሰታን እንጾማለን፤ የምንችል ደግሞ አስቀድሰን ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን እንቀበላለን፡፡ በተጨማሪም ይህ ጾም ለእመቤታችን ያለንን ፍቅርም የምንገልጽበት ወቅት ነው፡፡ በተለይ ኦርቶዶክሳውያን ሕፃናት በአብዛኛው ትምህርተ ወንጌል የሚማሩት፤ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን የሚቀበሉት በዚህ በጾመ ፍልሰታ ነው፡፡

 

ኹላችንም ጌታችን በስሙ ሁለትም ሦስትም ኾነን ለጸሎትና ለመልካም ሥራ ብንሰባሰብ እርሱ በመካከላችን እንደሚገኝ የገባልንን ቃል ኪዳን መሠረት በማድረግ /ማቴ.፲፰፥፳/ በጾመ ፍልሰታ ሳምንታት በጌታችን፣ በእመቤታችንና በቅዱሳን ሐዋርያት ስም በቤተ ክርስቲያን ተሰባስበን ቅዱሳት መጻሕፍትን ከመማር ባሻገር ብንጾም፣ ብንጸልይ፣ ብናስቀድስ፤ እንደዚሁም ሥጋውን ደሙን ብንቀበል በበረከት ላይ በረከትን፤ በጸጋ ላይ ጸጋን እናገኛለን፡፡ በኋላም ሰማያዊውን የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ እንችላለን፡፡

 

ነገር ግን በሕግ የተከለከለ እስኪመስል ድረስ በዚህ ወቅትም ኾነ በሌላ ጊዜ ሥጋውን ደሙን የሚቀበሉ ወጣቶች ጥቂቶች ናቸው፡፡ ስለዚህም አረጋውያንና ሕፃናት ብቻ ሳይኾኑ ወጣቶችም ጭምር የመቍረብና የመዳን ክርስቲያናዊ መብት እንዳለን በመረዳት ራሳችንን ገዝተን፣ ንስሐ ገብተን፣ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን መቀበል ይገባናል፡፡ አምላካችን በማይታበል ቃሉ “ሥጋዬን የሚበላ፤ ደሜንም የሚጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው” በማለት ተናግሯልና /ዮሐ.፮፥፶፬/፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይኹን፡፡ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ሐዋርያት ጸጋና በረከት አይለየን፡፡

እናቴ ሆይ እሳቱን አትፍሪ፤ እግዚአብሔር ያድነናል፡፡

ሐምሌ ፲፰ ቀን፣ ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

007

በመጽሐፈ ስንክሳር እንደ ተመዘገበው ሐምሌ ፲፱ ቀን ቅዱስ ቂርቆስና ቅድስት ኢየሉጣ በሰማዕትነት መከራ የተቀበሉበትና ስማቸውን የሚጠራ፣ ዝክራቸውንም የሚዘክሩ ምእመናን ይቅርታን፣ ምሕረትን እንደሚያገኙ ከጌታችን ከመድኀኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ቃል ኪዳን የተቀበሉበት ዕለት ነው፡፡ እንደዚሁም እግዚአብሔር አምላካችን ቅዱስ ገብርኤልን ልኮ እነዚህን ቅዱሳን መርዳቱ የሚነገረው በዚሁ ዕለት ነው፡፡ የሰማዕታቱ ቅዱስ ቂርቆስና የኢየሉጣ ታሪክም በአጭሩ የሚከተለው ነው፤

 

አንጌቤን በሚባል አገር በክርስትና ሃይማኖት ጸንታ የምትኖርና እግዚአብሔርን የምትፈራ ቅድስት ኢየሉጣ የምትባል ደግ ሴት ነበረች፡፡ ልጇን ቅዱስ ቂርቆስንም በሃይማኖትና በምግባር አሳድጋዋለች፡፡ የዘመኑን አረማዊ መኰንን እለእስክንድሮስን በመፍራት ከሮም ወደ ጠርሴስ ከልጇ ጋር በተሰደደች ጊዜ መኰንኑ እነርሱ ከሚገኙበት አገር ገብቶ ክርስቲያኖችን እያሳደደ መግደል ጀመረ፡፡

 

የንጉሡ ወታደሮችም ቅድስት ኢየሉጣንና ቅዱስ ቂርቆስን እግዚአብሔርን እንዲክዱ፤ ለጣዖት እንዲሰግዱ ቢያፈስራሯቸውም ቅዱሳኑ ግን ሃይማኖታቸውን ለመለወጥ ፈቃደኛ አልኾኑም፡፡ በዚህም መኰንኑ ተቈጥቶ ጨውና ሰናፍጭ በዓይንና በአፍንጫቸው ውስጥ በመጨመር፤ በጋሉ የብረት ችንካሮች በመቸንከርና መላ ሰውነታቸውን በመብሳት በብዙ ዓይነት መሣሪያ አሠቃያቸው፡፡ እግዚአብሔርም የጋሉ ብረቶችን እንደ ውኀ ያቀዘቅዝላቸው፤ ሥቃያቸውንም ያቀልላቸው ነበር፡፡

 

በሌላ ጊዜም በገመድ አሳሥሮ ሲያስጨንቃቸው ከቆየ በኋላ ራሳቸውን ከቆዳቸው ጋር አስላጭቶ እሳት አነደደባቸው፡፡ ዳግመኛም ከትከሻቸው እስከ እግራቸው ድረስ በሚደርሱ ችንካሮች በቸነከራቸው ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ተልኮ ከሥቃያቸው አድኗቸዋል፡፡ አሁንም ቀኑን ሙሉ በልዩ ልዩ የሥቃይ መሣሪያዎች ቢያስጨንቃቸውም የእግዚአብሔር ኃይልና የቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት አልተለያቸውም ነበርና ምንም ዓይነት ጉዳት አልደረሰባቸውም፡፡

 

እንደገናም በመጋዝ ሰንጥቀው በብረት ምጣድ በቆሏቸው ጊዜ ጌታችን ከሞት አነሣቸውና በመኰንኑ ፊት ድንቅ ተአምራትን አደረጉ፡፡ ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ የመኰንኑን ጫማ በጸሎት ወደ በሬነት እንዲቀየር ባደረገ ጊዜም መኰንኑ በተአምራቱ በመቈጣቱ ምላሱን ቢያስቈርጠውም ጌታችን ምላሱን አድኖለታል፡፡

 

ዳግመኛም በፈላ የጋን ውሃ ውስጥ ቅዱሳን ቂርቆስና ኢየሉጣን ሊጨምሯቸው ሲሉ ቅድስት ኢየሉጣ በፈራች ጊዜ ቅዱስ ቂርቆስ “እናቴ ሆይ አትፍሪ፤ አናንያ፣ ዓዛርያና ሚሳኤልን ከእሳት ነበልባል ያዳናቸው እግዚአብሔር እኛንም ከዚህ የፈላ ውሃ ያድነናል” እያለ ያረጋጋትና በተጋድሎዋ እንድትጸና ወደ እግዚአብሔር ይጸልይላት ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ተያይዘው ወደ ጋኑ ውስጥ ገቡ፡፡ ያ ውሃም እንደ ውርጭ ቀዘቀዘ፡፡ ደግሞም ወታደሮቹ መንኰራኵር ባለበት የብረት ምጣድ ውስጥ ከተው ሥጋቸው እስኪቈራረጥ ድረስ በጎተቷቸው ጊዜም ቅዱስ ገብርኤል በሕይወት አድኗቸዋል፡፡

 

በአጠቃላይ ቅዱስ ቂርቆስና ቅድስት ኢየሉጣ የዚህን ዓለም ጣዕም በመናቅ “ሞት ቢኾን፣ ሕይወትም ቢኾን፣ መላእክትም ቢኾኑ፣ ግዛትም ቢኾን፣ ያለውም ቢኾን፣ የሚመጣውም ቢኾን፣ ኃይላትም ቢኾኑ፣ ከፍታም ቢኾን፣ ዝቅታም ቢኾን፣ ልዩ ፍጥረትም ቢኾን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ካለ ከእግዚአብሔር ፍቅር ሊለየን እንዳይችል ተረድቼአለሁ፤” /ሮሜ.፰፥፴፰-፴፱/ ሲል ቅዱስ ጳውሎስ የተናገረውን ቃል በተግባር በማሳየት ለክርስቶስ ፍቅር ሲሉ ራሳቸውን ለመከራና ለሞት አሳልፈው ሰጥተዋል፡፡

 

በመጨረሻም ከእግዚአብሔር ቃል ኪዳን ተቀብለው በመንፈቀ ሌሊት አንገታቸውን ተቈርጠው በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ እስከ ሞት ድረስ በታመኑበት ተጋድሏቸውም ከእግዚአብሔር ዘንድ የሕይወትን አክሊል ተቀብለዋል፡፡ ተጋድሏቸውን እስኪፈጽሙ ድረስም ቅዱስ ገብርኤል አልተለያቸውም፡፡

 

በቅዱስ ገብርኤል ተራዳኢነት ቅድስት ኢየሉጣና ቅዱስ ቂርቆስ ብቻ ሳይኾኑ ብዙ ምእመናንም ተጠቅመዋል፡፡ ለዚህም ስሙ በሚጠራባቸው ገዳማትና አድባራት የሚያደርጋቸው ድንቅ ድንቅ ተአምራት ምስክሮች ናቸው፡፡ ይህም ቅዱሳን መላእክት በእግዚአብሔር ስም መከራ የሚቀበሉ ምእመናንን እንደሚጠብቁና ከልዩ ልዩ ደዌ እንደሚፈውሱ የሚያስረዳ ታሪክ ነው፡፡

 

እኛም በሃይማኖታችን ምክንያት መከራ ባጋጠመን ጊዜ ቈራጥ ልብ ያለው ሕፃኑ ቅዱስ ቂርቆስ “እናቴ ሆይ አትፍሪ” እያለ እናቱን በመከራ እንድትጸና እንዳረጋጋትና ለሰማዕትነት እንድትበቃ እንዳደረጋት ኹሉ፣ ዘለዓለማዊውን የእግዚአብሔርን መንግሥት በአንድነት ለመውረስ እንድንችል “አይዞህ! አይዞሽ! አትፍራ! አትፍሪ” በመባባል እስከ ሞት ድረስ በመታመን በዚህ ዓለም የሚገጥመንን መከራ በትዕግሥት ለማሳለፍ ቈርጠን መነሣት ይኖርብናል፡፡ ክርስትና ለብቻ የሚጸደቅበት መንገድ ሳይኾን ለኹላችንም የተሰጠ የጋራ የድኅነት በር ነውና፡፡

 

ከዚሁ ኹሉ ጋርም ቅዱስ ቂርቆስንና ቅድስት ኢየሉጣን የተራዳው የእዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል በአማላጅነቱ እንዲጠብቀን “በእግዚአብሔር ታምነን በቀንም በሌሊትም የአንተን ልመና ተስፋ እናደርጋለን” እያልን ዘወትር ልንማጸነው ያስፈልጋል፡፡ እርሱ ከፈጣሪው ከእግዚአብሔር በተሰጠው ቃል ኪዳን መሠረት ከሚደርስብን ልዩ ልዩ መከራና ሥቃይ ያድነናልና፡፡ “የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙሪያ ይሠፍራል፤ ያድናቸውማል፤” ተብሎ እንደ ተጻፈ /መዝ.፴፬፥፯/፡፡

 

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፡፡ እኛንም በቅዱስ ገብርኤል፣ በቅድስት ኢየሉጣና በቅዱስ ቂርቆስ ጸሎትና ምልጃ ይጠብቀን፡፡ የቅዱሳን ተራዳኢነት አይለየን፡፡

ሥላሴ በአብርሃም ቤት

ሐምሌ ቀን ፳፻፰ .

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሐምሌ ፯ ቀን እግዚአብሔር አምላክ በአብርሃም ቤት የገባበትና ሣራ ይስሐቅን እንደምትወልድ የተናገረበት ዕለት በመኾኑ በቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ በደማቅ ሥርዓት ይከበራል፡፡ ታሪኩም በአጭሩ እንዲህ ነው፤

 

አባታችን አብርሃም ከተመሳቀለ ጐዳና ድንኳን ሠርቶ መንገደኞችን ኹሉ በእንግድነት እየተቀበለ ሲያስተናግድ ይኖር ነበር፡፡ ጥንተ ጠላታችን ሰይጣን ለተንኮል አያርፍምና ይህንን መልካም ግብሩን ለማሰናክል አስቦ የተጐዳ ሰው መስሎ ከጐዳና ቆሞ ወደ አብርሃም ቤት የሚሔዱ እንግዶችን አብርሃም እንግዳ መቀበል እንደ ተወ፤ እርሱም ሊበላ ሊጠጣ ከቤቱ ቢሔድ ራሱን ፈንክቶ፣ ደሙን አፍሶ፣ አጥንቱን ከስክሶ፣ ልብሱን ገፎ እንደ መለሰው አድርጎ እየተናገረ እንግዳ ወደ ቤቱ እንዳይመጣ አደረገ፡፡ አብርሃምም ማዕደ እግዚአብሔርን ያለ ምስክር (ያለ እንግዳ) አልመገብም ብሎ ሦስት ቀን ሳይመገብ ጾሙን አደረ /ቅዳሴ ማርያም አንድምታ ትርጓሜ/፡፡

 

በሦስተኛው ቀን እግዚአብሔር በሦስት ሰዎች ተመስሎ ከአብርሃም ቤት ገብቷል፡፡ በኦሪት ዘፍጥረት ተጽፎ እንደምናገኘው በቀትር ጊዜ አብርሃም በድንኳኑ ደጃፍ ተቀምጦ ሳለ እግዚአብሔር በመምሬ አድባር ዛፍ ለአብርሃም ተገልጦለታል፡፡

 

አብርሃምም ሦስት ሰዎች ቆመው ባየ ጊዜ ሊቀበላቸው ከድንኳኑ ደጃፍ ተነሥቶ ወደ እነርሱ ሮጠ፡፡ ወደ ምድርም ሰገደና አቤቱ በፊትህስ ሞገስ አግኝቼ እንደ ኾነ ባሪያህን አትለፈኝ? ብሎ ተማጸነ፡፡ እዚህ ላይ ሦስት ሰዎች፣ሊቀበላቸው፣ወደ እነርሱ፣…” የሚሉት ሐረጋት ሦስትነቱን፤ በፊትህስ ሞገስ አግኝቼ እንደ ኾነ ባሪያህን አትለፈኝ? የሚለው ዐረፍተ ነገር ደግሞ አንድነቱን ያመለክታል፡፡

 

በመቀጠልም አብርሃም ጥቂት ውኃ ይምጣላችሁ፤ እግራችሁን ታጠቡ፤ ከዚህችም ዛፍ በታች ዕረፉ፡፡ ቍራሽ እንጀራም ላምጣላችሁ፤ ልባችሁንም ደግፋ ከዚያም በኋላ ትሔዳላችሁ ስለዚህ ወደ ባሪያችሁ መጥታችኋልና ሲላቸው እነርሱም እንዳልህ አድርግ ብለውታል፡፡

 

በዚህ ኃይለ ቃልም የእግዚአብሔርን ሦስትነት እንረዳለን፡፡ የዘፍጥረት አንድምታ ትርጓሜ እንደሚያስረዳው አብርሃም ሥላሴን ጌቶቼ ከቤት ገብታችሁ ዕረፉ ሲላቸው ደክሞናልና አዝለህ አስገባን ብለውታል፡፡ እርሱም እሺ ብሎ አንዱን አዝሎ ቢገባ ሁለቱ በግብር አምላካዊ ከቤቱ ገብተዋል፡፡

 

አብርሃምም ወደ ሣራ ዘንድ ፈጥኖ ገባና ሦስት መሥፈሪያ ዱቄት ፈጥነሽ አዘጋጂ፤ ለውሺውም፤ እንጎቻም አድርጊ አላት፡፡ እርሷም እንዳዘዛት አደረገች፡፡ ሦስት መሥፈሪያ የሦስትነት፤ ዳቦው አንድ መኾኑ የአንድነት ምሳሌ ነው፡፡ አብርሃምም ወደ ላሞቹ ሔዶ ወይፈን አምጥቶ አርዶ አወራርዶ አዘገጅቶላቸው ተመግበዋል፡፡

 

ወይፈኑም ተነሥቶ ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ ብሎ እግዚአብሔርን አመስገኗል፡፡ ነገር ግን ሥላሴ በሰው አምሳል ስለ ተገለጡና ለአብርሃም የበሉ መስለው ስለ ታዩት ተመግበዋል ተባለ እንጂ ለሥላሴ መብል መጠጥ የሚስማማቸው ኾኖ አይደለም፡፡ መምህራነ ቤተ ክርስቲያን እንዳስተማሩን ሥላሴ ምግብ በሉ ማለት ቅቤ ከእሳት ገብቶ አልቀለጠም እንደ ማለት ነው፡፡

 

ከዚያ በኋላ እግዚአብሔር አብርሃምን ጠርቶ ሚስትህ ሣራ ወዴት ናት?” አለው፡፡ አብርሃምም ከድንኳኑ ውስጥ እንዳለች ነገረው፡፡ እዚህ ላይ እግዚአብሔር ሣራ ወዴት ናት?” ሲል መጠየቁ ያለችበት ጠፍቶበት ሳይኾን የሚነግራት ታላቅ የምሥራች እንዳለ ለማጠየቅ ነው፡፡ ይኸውም አዳም ወዴት ነህ?” ከሚለው ጥያቄ ጋር ተመሳሳይነት አለው /ዘፍ.፫፥፱/፡፡

 

እግዚአብሔር አምላክ አባታችን አዳምን ወዴት ነህ?” ሲል የጠየቀው ያለበትን ዐላውቅ ብሎ ሳይኾን ቃል በቃል ሊያነጋግረውና ከልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ የሚለውን ቃል ኪዳን ሊገባለት ነበር፡፡ እንደ አዳም ኹሉ ለሣራም ለጊዜው ይስሐቅን እንደምትወልድ፤ ለፍጻሜው ግን እግዚአብሔር ከአብርሃም ወገን ከምትኾን ከቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋ ለብሶ እንደሚገለጥና ዓለምን እንደሚያድን ለመንገር አብርሃምን ሚስትህ ሣራ ወዴት ናት? ሲል ጠይቆታል፡፡

 

እግዚአብሔርም የዛሬ ዓመት እንደ ዛሬው ጊዜ ወደ አንተ በእውነት እመለሳለሁ፤ ሚስትህ ሣራም ልጅን ታገኛለችብሎ ለአብርሃም ነገረው፡፡ ሣራ ይህንን ቃል በሰማች ጊዜ ባለቤቷም አርጅቶ፤ እርሷም የሴቶች ግዳጅ ትቷት ነበርና ሲያረጁ አምባር ይዋጁ እንዲሉ እስከ ዛሬ ድረስ ቆንጆ ነኝን? ጌታዬ አብርሃምስ ገና ጐረምሳ ነውን?” ብላ በመጠራጠሯ ሳቀች፡፡

 

እግዚአብሔርም አብርሃምን ሣራ ለምን ትስቃለች? በውኑ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር አለን?” አለው፡፡ ይህንን ኃይለ ቃልም እመቤታችንን በድንግልና ፀንሳ በድንግልና እንደምትወልድ ሲያበሥራት ወንድ ሳላውቅ ይህ እንዴት ሊኾን ይችላል?” ብላ በጠየቀችው ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ተናግሮታል /ሉቃ.፩፥፴፯/፡፡

 

ሣራም ስለፈራች አልሳቅሁም” አለች፡፡ እግዚአብሔርም መሳቋን እንዳወቀባት ከነገራት በኋላ በድጋሜ በዓመቱ ወደ አብርሃም ቤት እንደሚመጣና ሣራ ወንድ ልጅ እንደምትወልድ (ይስሐቅን) አብሥሯቸዋል፡፡ ይህም አምስት ሺሕ ከአምስት መቶ ዓመት ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ ሥጋ ለብሼ በመጣሁ ጊዜ ሣራ ወንጌል ምእመናንን ታስገኛለች ማለትም ሐዲስ ኪዳን ተመሥርታ ክርስቲያኖችን ታፈራለች ሲለው ነው፡፡

 

የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት እንደ ተረጐሙልን የአብርሃም ድንኳን የእመቤታችን ምሳሌ ነው፤ ቀትር በኾነ ጊዜ ማለትም በስድስት ሰዓት አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ወደ አብርሃም ድንኳን እንደ ገቡ ኹሉ፣ አምስት ሺሕ አምስት መቶው ዓመት ተፈጽሞ በስድስተኛው ሺሕ ዓመት እግዚአብሔር አብ ለአጽንዖ፤ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ለአንጽሖ፤ እግዚአብሔር ወልድ በተለየ አካሉ ሥጋን ለመልበስ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም አድረዋል፡፡ “በስድስተኛው ወር ቅዱስ ገብርኤል ከእግዚአብሔር ዘንድ ወደ እመቤታችን ተላከ፤” እንዳለ ቅዱስ ወንጌል /ሉቃ.፩፥፳፮/፡፡

 

ስድስተኛው ወር የሚለው ሐረግ በአንድ በኩል ጌታችን የተፀነሰበት ወርኃ መጋቢት ስድስተኛው ወር መኾኑንና (ከጥቅምት ጀምሮ በመቍጠር)፤ ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት በተፀነሰ በስድስተኛው ወር ጌታችን መፀነሱን፤ በሌላ በኩል ደግሞ አምስት ሺሕ አምስት መቶው ዘመን ተፈጽሞ በስድስተኛው ሺሕ ዘመን ቅዱስ ገብርኤል ወደ እመቤታችን መላኩን ያመለክታል /ትርጓሜ ወንጌል/፡፡

 

በአብርሃም ቤት (በድንኳኑ) ውስጥ ወይፈኑ ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ ብሎ እንዳመሰገነ ኹሉ እግዚአብሔር አምላክ ከእመቤታችን በተወለደ ጊዜም ቅዱሳን መላእክትና የሰው ልጅ በአንድነት ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ሥምረቱ ለሰብእ፤ ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይኹን፤ ሰላምም በምድር፤ ለሰውም በጎ ፈቃድ እያሉ እግዚአብሔርን አመስግነዋል /ሉቃ.፪፥፲፬/፡፡

 

እግዚአብሔር አምላክ ለአብርሃም የይስሐቅን መወለድና በሥጋ ማርያም መገለጡን ከነገረው በኋላ ተመልሶ ሔዷል፡፡ ሔዷል ስንልም ሥላሴ ከአብርሃም ቤት ሲወጡ መታየታቸውን ለማመልከት እንጂ እግዚአብሔር መሔድ መምጣት የሚነገርለት ኾኖ አይደለም፡፡ እርሱ በዓለሙ ኹሉ ሰፍኖ የሚኖር አምላክ ነውና፡፡ ነገር ግን በልዩ ልዩ ምሳሌ እየተገለጠ ጸጋውን፣ በረከቱን ማሳደሩን ለመግለጽ መጣ፤ ሔደ፤ ወረደ፤ ዐረገ እየተባለ ይነገርለታል፡፡

/ምንጭ፡- የኦሪት ዘፍጥረት አንድምታ ትርጓሜ፣ ምዕ. ፲፰፥፩-፲፱/፡፡

 

ሐምሌ ፯ ቀን እግዚአብሔር በአብርሃም ቤት ተገኝቶ የይስሐቅን መወለድና የእግዚአብሔርን ሰው መኾን ከመናገሩ በተጨማሪ የአብርሃምን ዘሩን እንደሚያበዛለትና አሕዛብ ኹሉ በእርሱ እንደሚከብሩ ማለትም ከአብርሃም ዘር በተገኘው በኢየሱስ ክርስቶስ አሕዛብ እንደሚቀደሱና ይህንን ምሥጢርም እግዚአብሔር ከወዳጁ ከአብርሃም እንደማይሠውር ቃል የገባለት ቀን ነው፡፡ በተጨማሪም እግዚአብሔር በኀጢአታቸው የተነሣ ሰዶምንና ገሞራን ያጠፋው፤ አብርሃምም በአማላጅነት በፊቱ የቆመው በዛሬው ዕለት ነው፡፡

 

ከዚህ ታሪክ እግዚአብሔር እንደ አብርሃም ልቡናቸው ቅን በኾነና በለጋሾች ማለትም ምጽዋትንና እንግዳ መቀበልን የዘወትር ልማዳቸው አድርገው በሚኖሩ ሰዎች ቤት እንደሚገኝ፤ እግዚአብሔር በረድኤቱ ወደ ሰው ቤት ሲገባም የተዘጋ ማሕፀን እንደሚከፍትና ቤቱን በበረከት እንደሚሞላ፤ እንደዚሁም የተሠወረ ምሥጢር እንደሚገልጽ እንረዳለን፡፡ ለዚህም እግዚአብሔር በአብርሃም ቤት ገብቶ ያደረገው ኹሉ ትልቅ ማስረጃ ነው፡፡ ከዚሁ ኹሉ ጋርም እግዚአብሔር አምላክ በአንድነቱም በሦስትነቱም እየታየ አምላክነቱን ለዘመናት እንደሚገልጥና የቸርነቱን ሥራ እንደሚሠራም ከታሪኩ እንማራለን፡፡

 

ይህ የእግዚአብሔር በአብርሃም ቤት መገለጥም በአንድ ወቅት ብቻ የተፈጸመና ነበር እየተባለ የሚነገር ታሪክ ሳይኾን፣ ለዘለዓለሙ ሲነገርና ሲፈጸም የሚኖር ሕያው ትምህርት ነው፡፡ ይህንንም እግዚአብሔር ለቅዱሳኑ በልዩ ልዩ መንገድ እየተገለጠ ለዘመናት በሚያደርገው ድንቅ ሥራና ተአምር መገንዘብ እንችላለን፡፡

 

ዛሬም ሀብት ንብረት ያለን ምእመናን በትሩፋት ሥራ በመሠማራት ማለትም እንግዶችን በመቀበል፣ ለተራቡ በማብላት፣ በመመጽወት ተግባር ከኖርን፤ በቂ ንብረት የሌለን ደግሞ ልቡናችንን ንጹሕ ከማድረግና ከኀጢአት ከመራቅ በተጨማሪ ቤት ላጡና ለተቸገሩ መራራትን፣ ደግነትን፣ ቀና አስተሳሰብን ገንዘብ ካደረግን እግዚአብሔር በሕይወታችን ውስጥ ያድራል፡፡ አድሮም ይባርከናል፤ ይቀድሰናል፡፡ በአጠቃላይ የምንሻውን መልካም ነገር ኹሉ ይፈጽምልናል፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

 

የብርሃናተ ዓለም ጴጥሮስና ጳውሎስ ዕረፍት

ሐምሌ ፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሐምሌ ፭ ቀን በአንድ በኩል የብርሃናተ ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ በዓለ ዕረፍት የሚዘከርበት ዕለት ሲኾን፣ በሌላ በኩል ደግሞ የጾመ ሐዋርያት ፋሲካ የሚከበረውም በዚሁ ዕለት ነው፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን የእነዚህን ቅዱሳን ታሪክ በአጭሩ ይዘንላችሁ ቀርበናል፤

ቅዱስ ጴጥሮስ

ጴጥሮስ ማለት በግሪክ ቋንቋ ዓለት (መሠረት) ማለት ነው፡፡ ወላጆቹ ስምዖን ይሉት ነበር፡፡ በአባቱ የሮቤል፣ በእናቱ የስምዖን ነገድ ሲኾን፣ የተወለደውም በገሊላ አውራጃ በቤተ ሳይዳ ነው፡፡ ሰዎችን በወንጌል መረብ እያጠመደ ወደ ክርስትና ሕይወት ይመልስ ዘንድ ጌታችን ከዓሣ አጥማጅነት ለሐዋርያነት ጠርቶታል /ሉቃ.፭፥፲፤ ማር.፩፥፲፮/፡፡ በመንፈሳዊ ቅንዓቱና ለጌታችን በነበረው ፍቅር የሐዋርያት አለቃ ኾኖ ተሹሟል፡፡ ለአገልግሎት ከተጠራበት ጊዜ ጀምሮም በእስያ፣ በሮም፣ በሰማርያ፣ በልዳ፣ በኢዮጴ፣ በአንጾኪያ፣ በገላትያና በሌሎችም አገሮች እየተዘዋወረ ወንጌልን ሰብኳል፡፡ በስብከቱ ምክንያትም ልዩ ልዩ መከራን ተቀብሏል፡፡ በቃል ካስተማረው ትምህርት በተጨማሪ በመጽሐፍ ቅዱስ በስሙ የተመዘገቡ ሁለት መልእክታትን ጽፏል፡፡

በመጨረሻም የክርስቲያኖች ጠላት የነበረው የሮም ንጉሥ ወደ አካይያ ዘምቶ ድል አድርጎ በደስታ ወደ ሮሜ ሲመለስ መኳንንቱን ለማስደሰት፤ ጣዖታቱንም ለማክበር ሲል በቅዱስ ጴጥሮስና በሌሎችም ክርስቲያኖች ላይ የሞት ፍርድ ዐወጀ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ በሮም ሲያስተምር ቆይቶ የሮም መኳንንት እንዳይገድሉት ትጥቁን ለውጦ ከሮም ሲወጣ ጌታችን መስቀል ተሸክሞ ተገለጸለት፤ በዚህ ጊዜ *አቤቱ ጌታ ሆይ ወዴት ትሔዳለህ? ሲል ቢጠይቀው ጌታችንም *ልሰቀል ወደ ሮም እሔዳለሁ* አለው፡፡ *ዳግመኛ ትሰቀላለህን?* ባለው ጊዜም *አንተ ሰትፈራ ጊዜ ነው እንጂ* አለው፡፡ ያን ጊዜም *ጐልማሳ ሳለህ ወገብህን ታጥቀህ ወደ ወደድኸው ትሔድ ነበር፡፡ ስትሸመግል ግን እጅህን ታነሣና ሌላ ሰው ያስታጥቅሃል፤ ወደማትወደውም ይወስድሃል፤* /ዮሐ.፳፩፥፲፰/ በማለት ጌታችን የነገረው ቃል ትዝ አለውና አሟሟቱን የሚያመለክት መኾኑን አስታውሶ ወደ ሮም ተመልሶ ወንጌልን መስበኩን ቀጠለ፡፡

በሮማውያን ሕግ ቅጣት የተፈረደበት ወንጀለኛ የሮም አገር ተወላጅ ከኾነ የወንጀሉ ክብደትና ቅለት እየታየ ግርፋት ወይም ሞት ይፈረድበት ነበር እንጂ በአንድ ወንጀል ሁለት ቅጣት አይቀጣም ነበር፡፡ ወንጀለኛው የውጪ አገር ዜጋ (ከሮም ውጪ) ከኾነ ግን ለምሳሌ ቅጣቱ ግርፋት ከኾነ ከተገረፈ በኋላ እስራት ይጨመርበታል፤ ቅጣቱ ሞት ከኾነም ከገረፉት በኋላ በመስቀል ወይም በሌላ መሣሪያ ይገድሉት ነበር፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ዜግነቱ ሮማዊ አልነበረምና በግርፋትም፣ በእስራትም በሞትም እንዲቀጣ ተፈረደበት፡፡

እንደ ሥርዓታቸውም አስቀድመው ከገረፉት በኋላ ሊሰቅሉት ሲሉ ወታደሮቹን *እንደ ክብር ንጉሥ እንደ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ አቁማችሁ ሳይኾን፣ ዘቅዝቃችሁ ስቀሉኝ* አላቸው፡፡ እነርሱም እንዳላቸው አድርገው ሐምሌ ፭ ቀን ዘቅዝቀው ሰቅለውታል፡፡ በመስቀል ላይ ሳለም ተከታዮቹን በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ ካዘዛቸው በኋላ ነፍሱን ለእግዚአብሔር ሰጠ፡፡ ሥጋውንም ደቀ መዝሙሩ መርቄሎስ ሽቱ ቀብቶ፣ በነጭ ሐር ገንዞ ዛሬ ቫቲካን በምትባለዋ ስፍራ በክብር ቀብሮታል፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ

ቅዱስ ጳውሎስ ለአገልግሎት ከመጠራቱ በፊት ሳውል ይባል ነበር፡፡ ከኦሪቱ ምሁር ከገማልያል ሕገ ኦሪትንና መጻሕፍተ ነቢያትን ተምሯል፡፡ ለሕገ ኦሪት ቀናኢ ከመኾኑ የተነሣም የክርስቶስ ተከታዮችን ኹሉ ያሳድድ ነበር፡፡ ቅዱስ እስጢፋኖስ በድንጋይ ተደብድቦ ሲገደልም የገዳዮቹ ልብስ ጠባቂ ነበር /ሐዋ.፯፥፶፰፤ ፳፪፥፳/፡፡ ክርስቲያኖችን ለማሳደድ ወደ ደማስቆ ሲሔድ ለሐዋርያነት ተጠርቷል /ሐዋ.፱፥፩-፴፩፤ ፳፪፥፩-፳፩/፡፡ ለሐዋርያነት ከተጠራበት ጊዜ ጀምሮ በመላው ዓለም እየተዘዋወረ ወንጌልን በመስበክ ብዙዎችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አሳምኗል፡፡

ሲሰብክም ጣዖት አምላኪ፣ ሕመምተኛ፣ ችግረኛ፣ አረማዊና አይሁዳዊ እየመሰለ ብዙዎችን አስተምሮ ለእግዚአብሔር መንግሥት አቅርቧል /፩ኛቆሮ.፱፥፲፱-፳፫/፡፡ ወንጌልን በመስበኩ ምክንያትም ከአይሁድና ከአረማውያን ዘንድ ብዙ መከራና ስቃይ ደርሶበታል፡፡ ዐረብ፣ አንጾኪያ፣ እልዋሪቆን፣ ሊቃኦንያ፣ ሦርያ፣ ግሪክና ልስጥራን ካስተማረባቸው አገሮች ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ በቃል ካስተማረው ሌላ በመጽሐፍ ቅዱስ በስሙ የተመዘገቡ ፲፬ መልእክታት አሉት፡፡

አገልግሎቱን ሊፈጽም ሲልም የሮም ንጉሥ ኔሮን ቄሣር የክርስቲያኖች ቍጥር እየጨመረ የመጣው በቅዱስ ጳውሎስ ትምህርት በመማረካቸው ምክንያት መኾኑን ተረድቶ፤ ይልቁንም የቤተ መንግሥቱ ሰዎች ሳይቀር በቅዱስ ጳውሎስ በመማረካቸው ተቈጥቶ ቅዱስ ጳውሎስን ወደ ፍርድ ሸንጎው አስቀረበው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም በቀኝ እጁ ከሰንሰለቱ ጋር መስቀሉን ይዞ ንጉሡንና ወታሮቹን ሳይፋራ የኢየሱስ ክርስቶስን የእግዚአብሔር ልጅነትና አምላካዊ ሥልጣኑን ይመሰክር ነበር፡፡ ንጉሡም በቍጣ ይሙት በቃ ፈረደበት፡፡

ከላይ እንደ ተገለጸው ሮማውያን የሞት ፍርድ ሲፈርዱ የሚቀጣው ሰው የሌላ አገር ዜጋ ከኾነ ከፍርዱ ውጪ ተጨማሪ ቅጣት ይቀጡትና ይገድሉት ነበር፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ ግን የሮም ዜግነት ስለ ነበረው ሳይገርፉ በአንድ ቅጣት ብቻ በሰይፍ እንዲገደል ወስነውበታል፡፡ ወደሚገደልበት ስፍራ ሲወስዱትም በንግግሩና በአስተያየቱ ኹሉ ምንም ፍርኀት አይታይበትም ነበር፡፡ እንዲያውም በጦርነት ድል አድርጎና ማርኮ እንደ ተመለሰ ወታደር ይደሰት ነበር እንጂ፡፡ ለሚገድሉትም ይቅርታን ይለምን ነበር፡፡ በገዳዮቹና በተከታዮቹ ፊትም የክርስትና ሽልማቱ የእግዚአብሔር መንግሥት መኾኑን የሚያስገነዝብ ቃል እያስተማረ እግዚአብሔር የሚሰጠውን የጽድቅ አክሊል ለመቀበል ይቻኮል ነበር /፪ኛቆሮ.፬፥፮-፲፰/፡፡

ሊገድሉት ሲወስዱትም ከንጉሥ ኔሮን ወገን የኾነችውን የአንዲት ብላቴና መጐናጸፊያ *ዛሬ እመልስልሻለሁ* ብሎ ከተቀበላት በኋላ *መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ፤ ሩጫዬን ጨርሻለሁ፡፡ ሃይማኖቴን ጠብቄአለሁ፤ ወደፊትም የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል፤* በማለት በመልእክቱ እንደ ተናገረው /፪ኞጢሞ.፬፥፯-፰/፣ ፊቱን በንጉሡ ልጅ መጐናጸፊያ ተሸፍኖ አንገቱን በሰይፍ ተቀልቶ አገልግሎቱን በሰማዕትነት ፈጽሟል፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ራሱን ከአንገቱ ጋር ቢያደርጉት እንደ ቀድሞው ደኅና ኾኖላቸው በክብር ገንዘው ቀብረውታል፡፡

ሰያፊው ቅዱስ ጳውሎስን እንደ ገደለው ለመናገር ወደ ንጉሡ ሲመለስም ያቺ መጐናጸፊያዋን የሰጠችው ብላቴና *ጳውሎስ ወዴት አለ?* አለችው፡፡ እርሱም *ራሱን ተቈርጦ በመጐናጸፊያሽ ተሸፍኖ ወድቋል* ሲላት *ዋሽተሃል፤ እነሆ ጴጥሮስና ጳውሎስ በእኔ በኩል አልፈው ሔዱ፡፡ እነርሱም የመንግሥት ልብስ ለብሰዋል፡፡ በራሳቸውም በዕንቍ ያጌጡ አክሊላትን አድርገዋል፡፡ መጐናጸፊያዬንም ሰጡኝ፡፡ ይህችውም እነኋት፤ ተመልከታት* ብላ ሰጠቸው፡፡ ከእርሱ ጋራ ለነበሩትም አሳየቻቸው፡፡ አይተውም አደነቁ፤ ስለዚህም በጌታቻን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ፡፡

እኛም ቅዱሳን ሐዋርያት ያቆዩልንን የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ጠብቀን፣ በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተን እንድንኖርና በመጨረሻም የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ እንድንበቃ የቅዱሳኑ ጸሎት ይርዳን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡-

መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሐምሌ ፭ ቀን፤

ዜና ሐዋርያት፡፡

ቅዱስ ታዴዎስ ሐዋርያ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሐምሌ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

ሐምሌ ፪ ቀን ከ፲፪ቱ ሐዋርያት አንዱ የኾው የቅዱስ ታዴዎስ የዕረፍቱ መታሰቢያ በዓል ነው፡፡ ከመጽሐፈ ስንክሳርና ከገድለ ሐዋርያት ያገኘነውን የሐዋርያው ታዴዎስን ታሪክ በአጭሩ እነሆ፤

ቅዱስ ታዴዎስ አባቱ እልፍዮስ ይባላል /ማቴ.፲፥፫/፡፡ ሐዋርያው *ታዴዎስ ልብድዮስ*፣ *የያዕቆብ ልጅ ይሁዳ* እየተባለም ይጠራል /ሉቃ.፮፥፲፮፤ ዮሐ.፲፵፥፳፪፤ ሐዋ.፩፥፲፫፤ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት/፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሐዋርያት አስቀድሞ ቅዱስ ታዴዎስን እንደ መረጠው መጽሐፈ ስንክሳር ይናገራል፡፡

ቅዱስ ታዴዎስ በየአገሩ እየተዘዋወረ ወንጌልን በመስበክ ከአይሁድና ከአረማውያን ወገን ብዙዎችን በክርስትና ሃይማኖት አሳምኖ አስጠምቋል፡፡ አንድ ቀን ወደ ሀገረ ስብከቱ ወደ ሦርያ ለስብከተ ወንጌል ሲሔድ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በጐልማሳ አምሳል ተገልጦ *ወዳጄ ታዴዎስ ሆይ፣ እኔ ከአንተ ጋር ነኝና አትፍራ* ብሎ ሰላምታ ሰጥቶት ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም የሐዋርያት አለቃ ነውና እንደ አባትነቱ ወደ ሦርያ ለማድረስ አብሮት ሔዶ ነበረ፡፡ ከከተማዋ አጠገብ ሲደርሱም አንድ ሽማግሌ በሮችን ጠምደው ሲያርሱ አገኙ፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም ሽማግሌውን ምግብ በለመናቸው ጊዜ *በሮቼን ጠብቁ* ብላዋቸው ምግብ ሊያመጡላቸው ወደ ቤታቸው ሔዱ፡፡

ሽማግሌው እስኪመለሱ ድረስም ቅዱስ ጴጥሮስ በሮችን ጠምዶ ሠላሳ ትልም ካረሰ በኋላ ቅዱስ ታዴዎስም በዚያ የነበረውን የሥንዴ ዘር መዝራት ጀመረ፡፡ የተዘራው ዘርም ወዲያዉኑ በቅሎ፣ አድጎ፣ እሸት ኾነ፡፡

ሽማግሌው ምግብ ይዘው ከቤታቸው ሲመለሱም ሐዋርያት ያደረጉትን ተአምር አይተው ደነገጡ፡፡ ከእግራቸው ሥር ወድቀው ለሐዋርያት ከሰገዱላቸው በኋላም *እናንተ ከሰማይ የወረዳችሁ አማልክት ናችሁን?* አሏቸው፡፡ እነርሱም *እኛ የእግዚአብሔር ባሮች እንጂ አማልክት አይደለንም* አሉ፡፡

ሽማግሌውም *ስላደረጋችሁልኝ በጎ ሥራ በምትሔዱበት ቦታ ኹሉ ልከተላችሁን?* ባላቸው ጊዜ *ይህንን ልታደርግ አይገባም፤ ነገር ግን በሮችን ለጌታቸው መልስና በቤትህ የምንበላውን ታዘጋጅልን ዘንድ ለባለቤትህ ንገራት፡፡ እኛ ወደዚህች ከተማ ገብተን እግዚአብሔር እስከሚጠራን ጊዜ ድረስ እንቆያለንና* አሏቸው፡፡

ሽማግሌውም ከሥንዴው እሸት ይዘው፣ በሮችን እየነዱ ወደ ከተማ ሲሔዱ የከተማው ሰዎች ወቅቱ የእርሻ እንጂ የእሸት ጊዜ አልነበረምና እየተገረሙ *ይህንን እሸት ከወዴት አገኘኸው?* አሏቸው፡፡ ሽማግሌው ግን ምላሽ አልሰጧቸውም ነበር፡፡

ሽማግሌው ሐዋርያት እንደዘዟቸው በሮችን ለጌታቸው መልሰው ቤታቸውን አዘጋጅተው ራት እንድታዘጋጅላቸው ለሚስታቸው ነገሩ፡፡

ወሬውን የከተማው መኳንንት በሰሙ ጊዜም ሽማግሌውን *በክፉ አሟሟት እንዳትሞት እሸቱን ከወዴት እንዳገኘኸው ንገረን* ብለው መልእክተኞችን ላኩባቸው፡፡ ሽማግሌውም *ሕይወት ከእኔ ጋራ ሳለ ሞትን አልፈራም* ካሉ በኋላ ሐዋርያት ያደረጉትን ኹሉ ነገሯቸው፡፡

መኳንንቱ *ሐዋርያቱን አምጣቸው* ሲሏቸውም ሽማግሌው ወደ እርሳቸው ቤት ሲመጡ ማግኘት እንደሚችሉ ነገሯቸው፡፡

መኳንንቱም ሰይጣን ልቡናቸዉን ስለ ለወጠው ሐዋርያቱን ለመግደል ተነሳሡ፡፡ እኩሌቶቹ ግን *አምላካቸው ኢየሱስ የሚሹትን ኹሉ እንደሚያደርግላቸው ሰምተናልና ልንገድላቸው አንችልም፡፡ ነገር ግን አመንዝራ ሴት ወስደን በከተማው በር ርቃኗን እናስቀምጣት፡፡ እርሷን ሲያዩ ወደ ከተማችን አይገቡም፤* አሉ፡፡

እንደተባባሉትም ሴትዮዋን በከተማው በር ርቃኗን አስቀመጧት፡፡ ሐዋርያው ታዴዎስ ባያት ጊዜም *ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ወደ ከተማው ገብተን በከበረ ስምህ እስክንሰብክ ድረስ ይህቺን ሴት በአየር ላይ ይሰቅላት ዘንድ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልን ላክልን* ብሎ ጸለየ፡፡

ጌታችን ጸሎቱን ተቀብሎት ሴትዮዋ በተሰቀለች ጊዜም የከተማው ሰዎችና መኳኳንንቱ ኹሉ እያዩአት *አቤቱ ፍረድልኝ* እያለች ትጮኽ ጀመር፡: መኳንንቱ ግን ሰይጣን ልቡናቸውን አጽንቶታልና የሐዋርያትን ትምህርት አልተቀበሉም፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ታዴዎስ ወደ እግዚአብሔር በጸለዩ ጊዜም ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤልን ልኮ የሰዎቹን ልቡና የማረኩ መናፍስትን ርኩሳንን አባረረላቸው፡፡ ሰዎቹም የሐዋርያትን ትምህርት ተቀብለው በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ፡፡

ሐዋርያው ታዴዎስም በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ካጠመቃቸው በኋላ ኤጰስ ቆጶሳትን፣ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው፡፡ በአየር ላይ የተሰቀለችውን ሴትም አውርዶ ዲያቆናዪት አደርጎ ሾማት፡፡

በሐዋርያት እጅም ብዙ ድንቆችና ተአምራት ተደረጉ፡፡ ዕውሮች አዩ፤ ሐንካሶች ቆመው ሔዱ፤ ዲዳዎች ተናገሩ፤ ደንቆሮዎች ሰሙ፤ ለምጻሞች ነጹ፤ አጋንንትም ካደሩባቸው ሰዎች እየወጡ ተሰደዱ፤ ሙታንም ተነሡ፡፡ የከተማው ሰዎችም ይህንን ተአምር አይተው በቅዱሳን ሐዋርያት አምላክ በእግዚአብሔር አመኑ፡፡

አንድ ሰይጣን ያደረበትና ገንዘብ የሚወድ ጐልማሳ ባለጸጋም ወደ ሐዋርያው ታዴዎስ መጥቶ ሰገደለትና *የእግዚአብሔር አገልጋይ ሆይ እድን ዘንድ ምን ላድርግ?* ሲል ጠየቀው፡፡

ሐዋርያው ታዴዎስም *እግዚአብሔርን በፍጹም ልብህ፣ በፍጹም ኀይልህ ውደደው፡፡ አትግደል፤ አትስረቅ፤ አታመንዝር፡፡ በአንተ ሊደረግብህ የማትሻውን በሌላው ላይ አታድርግ፡፡ ደግሞም ገንዘብህን ሸጠህ ለድኆችና ለምስኪኖች ብትሰጥ በሰማያት ለዘለዓለም የሚኖር ድልብ ታገኛለህ* አለው፡፡

ጐልማሳውም ይህንን በሰማ ጊዜ ተቈጥቶ ሐዋርያውን አነቀው፡፡ የእግዚአብሔር ኀይል በይረዳው ኖሮ ሐዋርያው ከመታነቁ ጽናት የተነሣ ዓይኖቹ ሊወጡ ነበር፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም *የክርስቶስን አገልጋይ እንዴት ደፍረህ ታንቃለህ?* ባለው ጊዜ ጐልማሳው ቅዱስ ታዴዎስን ለቀቀው፡፡

ያን ጊዜም ቅዱስ ታዴዎስ *ጌታችን ሀብታም መንግሥተ ሰማያት ከሚገባ ይልቅ ግመል በመርፌ ቀዳዳ ቢያልፍ ይቀላል ሲል በእውነት የተናገረው እንዳንተ ላለው ሀብታም ነው* አለው፡፡

ጐልማሳውም *ይህ ሊኾን አይችልም* ባለ ጊዜ ሐዋርያው ታዴዎስ በመንገድ ሲያልፍ ያገኘውን ባለ ግመል አስቁሞ መርፌ ገዝቶ ሊያሳየው ወደደ፡፡ መርፌ ሻጩም ሐዋርያውን ለመርዳት ፈልጎ ቀዳዳው ሰፊ የኾነ መርፌ አመጣለት፡፡

ቅዱስ ታዴዎስም *እግዚአብሔር ዋጋህን ይክፈልህ፤ ነገር ግን በዚህች አገር የእግዚአብሔር ክብር ይገለጥ ዘንድ ቀዳዳው ጠባብ የኾነ መርፌ አምጣልን* አለው፡፡

ሐዋርያው ቀዳዳው ጠባብ የኾነውን መርፌ ተቀብሎም *ኀይልህን ግለጥ* ብሎ ወደ ጌታችን ጸለየ፡፡ እጁንም ዘርግቶ ባለ ግመሉን *በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ከግመልህ ጋር በመርፌ ቀዳዳው ውስጥ እለፍ* አለው፡፡ ሰውየውም እስከ ግመሉ ድረስ በመርፌ ቀዳዳው አለፈ፡፡

ዳግመኛም *ሕዝቡ የፈጣሪያችንን የክርስቶስን ኀይል ይረዱ ዘንድ ዳግመኛ ገብተህ እለፍ* አለውና ሦስት ጊዜ በመርፌ ቀዳዳው አለፈ፡፡

ሕዝቡም ይህንን ተአምር አይተው *ከቅዱሳን ሐዋርያት አምላክ ከሕያው እግዚአብሔር ልጅ ከኢየሱስ በቀር ሌላ አምላክ የለም* እያሉ ድምፃቸውን ከፍ አድርገው ተናገሩ፡፡

ያ ጐልማሳ ባለጸጋም ከሐዋርያው ታዴዎስ እግር በታች ወድቆ ሰገደና *ኀጢአቴን ኹሉ ይቅር በለኝ፡፡ ገንዘቤንም ኹሉ ወስደህ ለድኆችና ለምስኪኖች አከፋፍልኝ* አለው፡፡ ሐዋርያውም እንደ ለመነው አደረገለት፡፡

የክርስትናን ሃይማኖትን ሕግ አስተምሮም አጠመቀውና ሥጋውንና ደሙን አቀበለው፡፡ ኹሉንም በቀናች የክርስትና ሃይማኖት አጸናቸው፡፡ ከዚያ በኋላም ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ታዴዎስ ከዚያች ከተማ ወጡ፤ ሕዝቡም በሰላም ሸኟቸው፡፡

ቅዱስ ታዴዎስ በየአገሩ እየተዘዋወረ ወንጌልን ሲሰብክ ቆይቶ ከአይሁድና ከአረማውያን ዘንድ ብዙ መከራ ከደረሰበት በኋላ አገልግሎቱን ፈጽሞ ሐምሌ ፪ ቀን በሰላም ዐርፏል፡፡

በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ዘመንም ሐምሌ ፳፱ ቀን የከበረ ዐፅሙ ከሦርያ ወደ ቍስጥንጥንያ ከተማ ፈልሷል፡፡ በዚያች ዕለትም ቤተ ክርስቲያን ሠርተው የቅዱሱን ዐፅም በውስጧ አስቀምጠውታል፡፡ ከዐፅሙም ብዙ ድንቆችና ተአምራት ተገልጠዋል፡፡

ኹላችንንም የሐዋርያው ጸሎት ይጠብቀን፤ በረከቱም ይደርብን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡-

መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሐምሌ ፪ እና ፳፱ ቀን፤

ገድለ ሐዋርያት፣ ፲፱፻፺፬ ዓ.ም፤ አዲስ አበባ፣ ገጽ ፻፷፭-፻፸፩፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት

ሰኔ ፴ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዝግጅት ክፍሉ

እንደሚታወቀው ሰኔ ፴ ቀን ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት የተወለደበት ዕለት ነው፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን የመጥምቁ ዮሐንስን ታሪክ በአጭሩ እናቀርብላችኋለን፤

ቅዱስ ዮሐንስ የካህኑ ዘካርያስና የቅድስት ኤልሳቤጥ ልጅ ሲኾን፣ የልደቱ ታሪክም እንዲህ ነው፤ በቅዱስ ሉቃስ ወንጌል እንደ ተገለጸው ካህኑ ዘካርያስ እና ሚስቱ ቅድስት ኤልሳቤጥ የእግዚአብሔር ትእዛዝ ኹሉ በመፈጸም ያለ ነቀፋ የሚኖሩ ጻድቃን ነበሩ፡፡ ኤልሳቤጥም መካን ነበረችና ልጅ አልነበራቸውም /ሉቃ.፩፥፭-፯/፡፡

ልጅ ይሰጣቸው ዘንድም እግዚአብሔርን ዘወትር ይማጸኑት ነበር፡፡ ካህኑ ዘካርያስ ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ ዕጣን በማሳረግ ላይ ሳለም የእግዚአብሔር መልአክ በዕጣኑ መሠዊያ ቀኝ ቆሞ ጸሎቱ እንደ ተሰማና ሚስቱ ቅድስት ኤልሳቤጥ እንደምትወልድ፤ ስሙንም ዮሐንስ እንደሚለው፤ በመወለዱም ብዙዎች እንደሚደሰቱ፤ ልጁም በእግዚአብሔር ፊት ታላቅ እንደሚኾንና የወይን ጠጅና የሚያሰክር መጠጥ እንደማይጠጣ፤ እንዲሁም ከእናቱ ማኅፀን ጀምሮ መንፈስ ቅዱስ እንደሚሞላበት ነገረው /ሉቃ.፩፥፰-፲፯/፡፡

ካህኑ ዘካርያስም *እኔ ሽማግሌ ነኝ፤ ሚስቴም በዕድሜዋ አርጅታለችና ይህን በምን አውቃለሁ?* አለው፡፡ መልአኩም *እኔ በእግዚአብሔር ፊት የምቆመው ገብርኤል ነኝ፤ እንድናገርህም ይህችንም የምሥራች እንድሰብክልህ ተልኬ ነበር፡፡ እነሆም በጊዜው የሚፈጸመውን ቃሌን ስላላመንህ ይህ ነገር እስከሚኾን ቀን ድረስ ዲዳ ትኾናለህ፤ መናገርም አትችልም፤* አለው፡፡ ከውጪ ቆመው ጸሎት ሲያደርጉ የነበሩት ሕዝብም ዘካርያስን ከቤተ መቅደስ እስኪወጣ ይጠብቁት ነበር፤ በመዘግየቱም ይደነቁ ነበር /ሉቃ.፩፥፲፰-፳፩/፡፡

ከቤተ መቅደስ በወጣም ጊዜ ሊያናግራቸው ባለመቻሉ ይጠቅሳቸው ነበር፡፡ በዚህም በቤተ መቅደስም ራእይ እንዳየ አስተዋሉ፡፡ እርሱም ድዳ ኾኖ ኖረ፡፡ የማገልገሉም ወራት ሲፈጸምም ወደ ቤቱ ሔደ፤ ከሁለት ቀን በኋላም አረጋዊቷ ቅድስት ኤልሳቤጥ ፀነሰች፡፡ ቅድስት ኤልሳቤጥም በመካንነቷ ከሰዎች የሚደርስባት ሽሙጥ ተወግዷላታልና *እግዚአብሔር በዚህ ወራት ከሰው ስድቤን ያርቅ ዘንድ እንዲህ አደረገልኝ* ስትል ለአምስት ወራት ተሸሸገች /ሉቃ.፩፥፳፪-፳፭/፡፡

ቅዱስ ገብርኤል እመቤታችን ጌታችንን በድንግልና እንደምትወልድ ሲያበሥራት *ወንድ ሳላውቅ ይህ እንዴት ሊኾን ይችላል?* ባለችው ጊዜ እግዚአብሔር ኹሉን ማድረግ እንደሚቻለው ለማስረዳት መካኗ ቅድስት ኤልሳቤጥ በስተእርጅና መውለዷን ጠቅሶላታል፡፡ ቅድስት ኤልሳቤጥ በፀነሰች በስድስተኛው ወር እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልትጠይቃት ወደ እርሷ በሔደች ጊዜም ቅዱስ ዮሐንስ በማኅፀን ውስጥ ኾኖ ለቅድስት ድንግል ማርያም እና በማኅፀኗ ላደረው አካላዊ ቃል (ለኢየሱስ ክርስቶስ) ሰግዷል /ሉቃ.፩፥፳፮-፵፩/፡፡

ቅድስት ኤልሳቤጥም ድምጿን ከፍ አድርጋ *አንቺ ከሴቶች መካከል የተባረክሽ ነሽ፤ የማኅፀንሽም ፍሬ የተባረከ ነው፡፡ የጌታዬ እናት ወደ እኔ ትመጣ ዘንድ እንዴት ይኾንልኛል? እነሆ የሰላምታሽን ድምፅ በሰማሁ ጊዜ ፅንሱ በማኅፀኔ በደስታ ዘሏልና፡፡ ከጌታ የተነገረላት ቃል እንደሚፈጸምላት ያመነች ብፅዕት ናት፤* በማለት እመቤታችንን አመስግናታለች /ሉቃ.፩፥፵፪-፵፭/፡፡ የመውለጃዋ ቀን ሲደርስም ሰኔ ፴ ቀን ንዑድ፣ ክቡር የኾነው መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ተወለደ። ዘመዶቹ የሕፃኑን ስም በአባቱ መጠሪያ *ዘካርያስ* ሊሉት ቢወዱም እናቱ ግን *ዮሐንስ ይባል* አለች፡፡

የመልአኩን የብሥራት ቃል ባለመቀበሉ አንደበቱ ተይዞ የነበረው ካህኑ ዘካርያም ስሙ *ዮሐንስ* ይባል ብሎ ሲጽፍ አፉ ተከፈተ፤ አንደበቱም ተፈታና በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ *… አንተ ሕፃን ሆይ የልዑል ነቢይ ትባላለህ፤ መንገዱን ልትጠርግ በጌታ ፊት ትሔዳለህና፡፡ የኃጢአታቸው ስርየት የኾነውን የመዳን ዕውቀት ለሕዝቡ ትሰጣለህ፡፡ ይህም ከላይ የመጣ ብርሃን በጐበኘበት በአምላካችን ምሕረትና ርኅራኄ ምክንያት ነው፡፡ ብርሃኑም በጨለማና በሞት ጥላ ተቀምጠው ላሉት ያበራል፤ እግሮቻችንንም በሰላም መንገድ ያቀናል፤* ብሎ ስለ ቅዱስ ዮሐንስ ነቢይነትና አጥማቂነት፣ እንደዚሁም የክርስቶስን የማዳን ትምህርት እንደሚያበሥር አስቀድሞ ትንቢት ተናገረ /ሉቃ.፩፥፶፯-፸፱/፡፡

ዮሐንስ ማለት *እግዚአብሔር ጸጋ ነው* ማለት ነው፡፡ ትርጓሜ ወንጌልም መጥምቀ መለኮት ዮሐንስን ፍሥሐ ወሐሴት (ተድላና ደስታ) ይለዋል፤ ወላጆቹ በእርሱ መወለድ ተደስተዋልና /ሉቃ.፩፥፲፬/፡፡

በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈ ሄሮድስ የመድኀኒታችን የክርስቶስን መወለድ ከሰብአ ሰገል ሲሰማ መንግሥቴን ይወስድብኛል ብሎ ስለ ሰጋ ጌታችንን ያገኘሁ መስሎት የቤተልሔም ሕፃናትን መግደል ጀመረ /ማቴ.፪፥፩-፲፮/፡፡ በዚህ ጊዜ ቅድስት ኤልሳቤጥ ልጇን ከሞት ለማዳን ስትል ሕፃኑ ዮሐንስን ይዛ ወደ በረሃ ተሰደደች። በበረሃም ድንጋይ ቤት ኾኖላቸው፣ እግዚአብሔርም ከብርድ፣ ከፀሐይና ከአራዊቱ አፍ እየጠበቃቸው መኖር ጀመሩ፡፡ ወደ በረሃ ሲገቡ ቅዱስ ዮሐንስ የሁለት ዓመት ከመንፈቅ ሕፃን ነበር፡፡ ሕፃኑም አደገ፤ በመንፈስም ጠነከረ፤ ለእስራኤል እስከታየበት ቀን ድረስ በምድረ በዳ ኖረ /ሉቃ.፩፥፹/፡፡

የሄሮድስ ጭፍሮችም ዮሐንስን ፈልገው ባጡት ጊዜ ዘካርያስን በቤተ መቅደስ ውስጥ በሰይፍ ገደሉት፤ ካህናቱም በንጹሕ ልብስ ገንዘው በአባቱ በበራክዩ መቃብር ቀበሩት፡፡ ደሙም እስከ ፸ ዓመት ድረስ ሲፈላ ኖረ። ጌታችንም የዘካርያስ ደም እንደሚፋረዳቸው ሲያስረዳ *ከአቤል ደም ጀምሮ በመሠዊያውና በቤተ መቅደስ መካከል እስከ ጠፋው እስከ ዘካርያስ ደም ድረስ ከዚህ ትውልድ ይፈለጋል* በማለት ጸሐፍት ፈሪሳውያንን ገሥጿቸዋል /ሉቃ.፲፩፥፶፩/፡፡

ቅድስት ኤልሳቤጥ ወደ በረሃ በገባች በአምስተኛ ዓመቷ፤ ቅዱስ ዮሐንስም ሰባት ዓመት ሲሞላው ሕፃኑን ከዚህ ዓለም ድካም ዐረፈች፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም እግዚአብሔር ከአራዊት አፍ እየጠበቀው፤ ሲርበው ሰማያዊ ኅብስትን እየመገበው ሲጠማውም ውኃ እያፈለቀ እያጠጣው፤ አናብስቱና አናምርቱ እንደ ወንድምና እኅት ኾነውለት በበረሃ መኖር ጀመረ፡፡ በበረሃ ሲኖርም የግመል ጠጉር ይለብስ፣ በወገቡም ጠፍር ይታጠቅ፣ አንበጣ (በአቴና ቀምሲስ፣ በኢትዮጵያ ሰበቦት /የጋጃ ማር/) የሚባል /የበረሃ ቅጠል/ እና መዓረ ጸደንያ /ጣዝማ ማር/ ይመገብ ነበር /ኢሳ.፵፥፫-፭/።

፴ ዓመት ሲሞላውም በነቢዩ በኢሳይያስ ቃል *… የጌታን መንገድ አዘጋጁ፤ ጥርጊያውንም አቅኑ፤ እያለ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ፡፡ ዐዘቅቱ ሁሉ ይሙላ፤ ተራራውና ኮረብታውም ኹሉ ዝቅ ይበል፡፡ ጠማማውም የቀና መንገድ ይኹን፤ ሸካራውም መንገድ ትክክል ይኹን፡፡ ሥጋም የለበሰ ኹሉ የእግዚአብሔርን ማዳን ይይ፤* ተብሎ እንደ ተነገረ ቅዱስ ዮሐንስ *መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ!* እያለ እየሰበከ በዮርዳኖስ ዙሪያ ወዳለው አገር ኹሉ ወጣ /ሉቃ.፫፥፫-፮/።

የይሁዳ አገር ሰዎች ኹሉ ኃጢአታቸውንም እየተናዘዙ ከእርሱ ይጠመቁ ነበር። እርሱም፡- *… እናንተ የእፉኝት ልጆች ከሚመጣው ቍጣ እንድትሸሹ ማን አመለከታችሁ? እንግዲህ ለንስሐ የሚገባ ፍሬ አድርጉ፤ መልካም ፍሬ የማያፈራ ዛፍ ኹሉ ይቈረጣል፤ ወደ እሳትም ይጣላል፤* ይላቸው ነበር፡፡ *ምን እናድርግ?* ብለው ሲጠይቁት *ሁለት ልብስ ያለው ለሌለው ያካፍል፤ ምግብም ያለው እንዲሁ ያድርግ፤* ይላቸው ነበር። ቀራጮችን፡- *ከታዘዘላችሁ አብልጣችሁ አትውሰዱ፤* ጭፍሮችንም፡- *በማንም ላይ ግፍ አትሥሩ፤ ማንንም በሐሰት አትክሰሱ፤ ደመወዛችሁም ይብቃችሁ፤* እያለና ሌላም ብዙ ምክር እየመከረ ወንጌልን ይሰብክላቸው ነበር /ሉቃ.፫፥፯-፲፬/፡፡

በተጨማሪም *… እኔ ለንስሐ በውኃ አጠምቃችኋለሁ፤ ነገር ግን የጫማውን ጠፍር መፍታት የማይገባኝ፣ ከእኔ በኋላ የሚመጣውና ከእኔ ይልቅ የሚበረታው እርሱ በመንፈስ ቅዱስና በእሳት ያጠምቃችኋል፤ መንሹም በእጁ ነው፤ አውድማውንም ፈጽሞ ያጠራል፤ ሥንዴውንም በጎተራው ይከታል፤ ገለባውን ግን በማይጠፋ እሳት ያቃጥለዋል* በማለት የክርስቶስን በሥጋ መገለጥ እና አምላክነት ነግሯቸዋል /ማቴ.፫፥፩-፲፪፤ ሐዋ.፲፫፥፳፬-፳፰/።

ቅዱስ ዮሐንስ ከፈሪሳውያን ወገን የኾኑ ካህናትና ሌዋውያን *ስለ ራስህ ምን ትላለህ?* ብለው በጠየቁት ጊዜም እርሱ ክርስቶስ እንዳልኾነና *የጌታን መንገድ አቅኑ* ብሎ በምድረ በዳ የሚጮኽ ቃለ ዐዋዲ (ዐዋጅ ነጋሪ) መኾኑን ተናግሯል /ሉቃ. ፫፥፲፭-፲፰፤ ዮሐ.፩፥፲፱-፳፫/።

ቅድስት ኤልሳቤጥ *የጌታዬ እናት ወደ እኔ ትመጣ ዘንድ እንዴት ይኾንልኛል?* /ሉቃ.፩፥፵፫/ ስትል እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክ መኾኗን እንደ መሰከረችው ኹሉ፣ ቅዱስ ዮሐንስ ጌታችን ሊጠመቅ ወደ እርሱ በሔደ ጊዜ *እኔ በአንተ ልጠመቅ ያስፈልገኛል፤ አንተም ወደ እኔ ትመጣለህን? ባሪያ ወደ ጌታው ይሔዳል እንጂ እንዴት ጌታ ወደ ባሪያው ይመጣል?* በማለት የጌታችንን አምላክነት በትሕትና ተናግሯል /ማቴ.፫፥፲፬/፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ጌታችንን *… ሌላውን በአንተ ስም አጠምቃለሁ፤ አንተንስ በማን ስም ላጥምቅህ?* ሲለው *እንደ መልከ ጼዴቅ ሹመት ሥልጣንህ ዘለዓለማዊ የኾነ የዓለሙ ካህን፤ የዓለምን ኃጢአት የምታስወግደው የእግዚአብሔር በግ፤ ብርሃንን የምትገልጽ የእግዚአብሔር አብ የባሕርይ ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ይቅር በለን?* እያልህ አጥምቀኝ ብሎት እንደታዘዘው አድርጎ አጥምቆታል፡፡ ቅዱስ ጌታችንን ባጠመቀው ጊዜ ከሰማይ *በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት፤* የሚለውን የእግዚአብሔር አብ ቃል መስማቱንና መንፈስ ቅዱስ በርግብ አምሳል መውረዱን በመመስከር ምሥጢረ ሥላሴን አስተምሯል /ማቴ.፲፯፥፭፤ ዮሐ.፩፥፴፬/፡፡

ጌታችንም፡- *ምን ልታዩ ወደ ምድረ በዳ ወጣችሁ? … ነቢይን? አዎን ይህ ከነቢይም ይበልጣል። (እነሆ መንገድህን በፊትህ የሚጠርግ መልክተኛዬን በፊትህ እልካለሁ) ተብሎ የተጻፈለት እርሱ ነው፤ ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሣም፤ ልትቀበሉትስ ብትወዱ ይመጣ ዘንድ ያለው ኤልያስ ይህ ነው፤ የሚሰማ ጆሮ ያለው ይስማ* በማለት የቅዱስ ዮሐንስን ታላቅነት ተናግሯል /ማቴ.፲፩፥፱-፲፩/።

ኤልያስ ፀጉራም እንደ ኾነ ኹሉ ዮሐንስም ልብሱ የግመል ፀጉር መኾኑ፤ ሁለቱም መናንያን፣ ጸዋምያን፣ ተሐራምያን (ፈቃደ ሥጋን የተዉ)፣ ዝጉሐውያን (የሥጋን ስሜት የዘጉ)፣ ባሕታውያን መኾናቸው፤ በተጨማሪም ኤልያስ አክአብና ኤልዛቤልን፣ ዮሐንስ ደግሞ ሄሮድስና ሄሮድያዳን መገሠፃቸው፤ ኤልያስ ከክርስቶስ ዳግም ምጽአት ቀድሞ እንደሚመጣ ኹሉ ዮሐንስም ከክርስቶስ ቀዳሚ ምጽአት (በአካለ በሥጋ መገለጥ) ቀድሞ ማስተማሩ ያመሳስላቸዋልና ጌታችን ዮሐንስን ኤልያስ ብሎታል። *እነርሱም ስለ ዮሐንስ እንደ ነገራቸው አስተዋሉ፤* ተብሎ እንደ ተጻፈ /ማቴ.፲፩፥፪-፲፱/።

በአጠቃላይ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ከአዲስ ኪዳን አበው አንዱ የኾነ፣ ንጹሓን ነቢያት፣ ቅዱስ ገብርኤልና አባቱ ዘካርያስ ትንቢት የተናገሩለት፣ ከሕፃንነቱ ጀምሮ ቅኑት እንደ ገበሬ፣ ጽሙድ እንደ በሬ ኾኖ እግዚአብሔርን ያገለገለ፣ በፍጹም ልቡ ዓለምን የናቀ፣ ከተድላዋና ከደስታዋም የተለየ፣ አምላክን ለማጥመቅ የታደለ ሐዋርያ፣ መምህር፣ ሰማዕት፣ ባሕታዊ፣ ነቢይ፣ ጻድቅ ነው፡፡

ሊቁም ከመላእክት፣ ከነቢያት፣ ከካህናት፣ ከሐዋርያት መካከል እንደርሱ መለኮትን ለማጥመቅ የተመረጠ አለመኖሩን በመጥቀስ *ዮሐንስ ከማከ ሶበ ፈተዉ ወጽሕቁ፤ እሳተ ነዳዴ ኢተክህሎሙ ያጥምቁ፤ ራጉኤል በትጋሁ ወኢዮብ በጽድቁ፤ ዮሐንስ ሆይ ራጉኤል በትጋቱ፣ ኢዮብም በጽድቁ ቢመኙም ሆነ ቢጨነቁ እንደ አንተ የሚነድ እሳትን (መለኮትን) ሊያጠምቁ አልተቻላቸውም* ሲል መስክሮለታል /መልክአ ዮሐንስ መጥምቅ፣ ለአዕይንቲከ/፡፡

በመጨረሻም መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ *ድንበር አታፍርሱ፤ ዋርሳ አትውረሱ፤* እያለ ንጉሡ ሄሮድስንና ሄሮድያዳን በመገሠፁ ምክንያት አንገቱን በሰይፍ ተቈርጦ በሰማዕትነት ካረፈ በኋላ የራስ ቅሉ ክንፍ አውጥቶ በዓለም እየተዘዋወረ ፲፭ አምስት ዓመት ወንጌልን አስተምሯል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ሰኔ ፴ ቀን የተወለደበት፤ መስከረም ፩ ቀን ቃል ኪዳን የተቀበለበት፤ መስከረም ፪ ቀን በሰማዕትነት ያረፈበት፤ ጥር ፲፩ ቀን ጌታችንን ያጠመቀበት፤ የካቲት ፴ ቀን ራሱ የተገኘችበት፤ ሚያዝያ ፲፭ ቀን ራሱ ያረፈችበት (ነፍሱ የወጣችበት)፤ ሰኔ ፪ ቀን ደግሞ ፍልሰተ ዐፅሙ (ዐፅሙ የፈለሰበት) በዓል በቤተ ክርስቲያናችን ይከበራል፡፡

የቅዱስ ዮሐንስ ሕይወቱና ትምህርቱ፣ ያደረጋቸው ድንቆችና ተአምራት፣ እንዲሁም እግዚአብሔር የሰጠው ቃል ኪዳንና ሰማዕትነቱ በገድሉ በሰፊው ተጽፏል፡፡ እኛም ክብሩን ለማስታወስ ያህል ይህንን አቀረብን፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይኹን፤ እኛንም በቅዱስ ዮሐንስ ጸሎት ይማረን፡፡ በረከቱም ይጠብቀን፡፡

ምንጭ፦ መጽሐፈ ስንክሳር፤

ትርጓሜ ወንጌል (ወንጌለ ሉቃስ)፤

ገድለ ዮሐንስ መጥምቅ፡፡

በአተ ክረምት

ሰኔ ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! በዛሬው ዝግጅታችን ስለ ዘመነ ክረምት መግባት፣ ሰኔ ፳፮ ቀን (በዕለተ ሰንበት) ስለሚነበቡ ምንባባትና ስለሚዘመረው መዝሙር የሚያስረዳ አጭር ጽሑፍ እንደሚከተለው ይዘንላችሁ ቀርበናል፤

*ክረምት* ከረመ፣ ከረመ ካለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲኾን፣ ትርጕሙም የዝናም፣ የአዝርዕት፣ የአረም ጊዜ፤ እንደዚሁም ዕፅዋት፣ አዝርዕትና አትክልት በቅለው፣ ለምልመው የሚያድጉበት፣ ምድር በአረንጓዴ ዕፀዋትና በልምላሜ የምታሸበርቅበት ወቅት ማለት ነው፡፡ በአተ ክረምት ስንልም የክረምት መግቢያ ማለታችን ነው፡፡ ይኸውም ከዚህ በኋላ ዘመነ ክረምት መጀመሩን ያመለክታል፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ከሰኔ ፳፭ እስከ መስከረም ፳፭ ቀን ድረስ ያለው ጊዜ ዘመነ ክረምት ይባላል፡፡ ዘመነ ክረምት ስለ ሥነ ፍጥረት ዘርዘር ባለ መልኩ የሚነገርበት፤ ፍጡርን ከፈጣሪ መናን (ምግብን) ከተመጋቢ ለይቶ የሚያሳይና የሚያሳውቅ ዘመን ነው፡፡

በዚህ ወቅት የውኃ ባሕርይ ይሰለጥናል፤ በመኾኑም ውኃ አፈርን ያጥባል፤ እሳትን ያጠፋል፡፡ ኾኖም ግን በብሩህነቱ ከእሳት፤ በቀዝቃዛነቱ ከነፋስ፤ በእርጥብነቱ ከመሬት ጋር ተስማምቶ ከሦስቱ ባሕርያት ጋር ይኖራል፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን በዚህ ወቅት በዕለተ ሰንበት (ሰኔ ፳፮ ቀን) የሚከተለው የቅዱስ ያሬድ መዝሙር ይዘመራል፤

ደምፀ እገሪሁ ለዝናም

ሶበ ይዘንም ዝናም ይጸግቡ ርኁባን

ደምፀ እገሪሁ ለዝናም

ሶበ ይዘንም ዝናም ይትፌሥሑ ነዳያን

ደምፀ እገሪሁ ለዝናም

ወሠርዐ ሰንበተ ለሰብእ ዕረፍተ

ደምፀ እገሪሁ ለዝናም

ደምፀ እገሪሁ ለዝናም

ይህ መዝሙር ወቅቱ የክረምት መግቢያ መኾኑንና የዝናምን መምጣት የሚያበሥር ሲኾን፣ በተጨማሪም ዝናም በሚዘንብበት ጊዜ የሚበቅለውን እህልና የምንጮችን መብዛት ተስፋ በማድረግ የተራቡ እንደሚጠግቡ፤ የተጠሙም እንደሚረኩ የሚያትት ምሥጢር ይዟል፡፡ እንደዚሁም ጊዜ ለበጋ፣ ጊዜ ለክረምት የሚሰጥ አምላክ ለሰው ልጅ ማረፊያ ትኾን ዘንድ ዕለተ ሰንበትን መፍጠሩንም ያስረዳል፡፡

በዚህ ሳምንት በዕለተ ሰንበት በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ ምንባባትም የሚከተሉት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ናቸው፤

፩ኛ ቆሮንቶስ ፲፭፥፴፫-፶፩

ፍሬ ዐሳቡ፡- አዝርዕት በስብሰው እንደሚበቅሉ ኹሉ የሰው ልጅም ከሞተ በኋላ ከሞት እንደሚነሣ፤ ሲነሣም እግዚአብሔር እንደ ሥራው መጠን ዋጋውን እንደሚከፍለው፤ እንደዚሁም የሰው ልጅ ሞቱንና የሚያገኘውን ሰማያዊ ዋጋ በማሰብ ከኀጢአት መለየት እንደሚገባው ያስረዳል፡፡

ያዕቆብ ፭፥፲፮-ፍጻሜ

ፍሬ ዐሳቡ፡- ነቢዩ ኤልያስ በጸሎት ዝናም እንዳይዘንምና እንደገና እንዲጥል ማድረጉን በመተረክ እኛም እምነቱ ካለን በጸሎት ኹሉን ማድረግ እንደሚቻለን ይናገራል፡፡

ግብረ ሐዋርያት ፳፯፥፲፩-፳፩

ፍሬ ዐሳቡ፡- ቅዱስ ጳውሎስና ተከታዮቹ መርከባቸው በማዕበል ክፉኛ መናወጧንና በእግዚአብሔር ኃይል መዳናቸውን፤ በባሕሩ ውስጥም በጨለማ ለብዙ ጊዜ መቆየታቸውን በማውሳት ይህ ወቅት (ዘመነ ክረምት) የውኃና የነፋስ ኃይል የሚያልበት ጊዜ መኾኑን ያስተምራል፡፡

ምስባክ፡- መዝሙር ፻፵፮፥፰

ኃይለ ቃሉ፡- *ዘይገለብቦ ለሰማይ በደመና ወያስተዴሉ ክረምተ ለምድር ዘያበቍል ሣዕረ ውስተ አድባር*

ፍሬ ዐሳቡ፡- እግዚአብሔር ሰማዩን በደመና የሚሸፍን፤ ዝናምንም (ክረምትን) ለምድር (ለሰው ልጅ) የሚያዘጋጅ፤ እንደዚሁም በተራሮች ላይ ሣርን (ዕፀዋትን) የሚያበቅል አምላክ መኾኑን ያስገነዝባል፡፡

ወንጌል፡- ሉቃስ ፰፥፩-፳፪

ፍሬ ዐሳቡ፡- ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቃለ እግዚአብሔርን በዘርዕ፣ የምእመናንን ልቡና (የመረዳት ዓቅም) ደግሞ በመንገድ፣ በዓለት፣ በእሾኽና በመልካም መሬት በመመሰል ቃሉን ሰምተው በሚለወጡትና በሚጠፉት መካከል ስላለው ልዩነት ማስተማሩን ያስረዳል፡፡

ቅዳሴው፡- ቅዳሴ ኤጲፋንዮስ ሲኾን ይህ ቅዳሴ ስለ ዝናም፣ ደመና፣ መብረቅ፣ ባሕርና መሰል ፍጥረታት ዑደት፤ እንደዚሁም እግዚአብሔር ዓለማትን በጥበቡ ፈጥሮ የሚገዛና የሚመግብ አምላክ መኾኑን ስለሚያብራራ በዘመነ ክረምት ይቀደሳል፡፡

በአጭሩ ሰኔ ፳፮ ቀን በሚከበረው ዕለተ ሰንበት በቤተ ክርስቲያን ከአዝርዕት፣ ከዝናም፣ ከልምላሜ፣ ከውኃ ሙላትና ከባሕር ሞገድ ጋር ተያያዥነት ያላቸው ትምህርቶች ከሰው ልጅ ሕይወትና ከምግባሩ እንደዚሁም በምድር ከሚያጋጥሙት ፈተናዎች ጋር እየተነጻጸሩ ይቀርባሉ፡፡

በአጠቃላይ ከሕይወታችን ጋር አያይዘን ስንመለከተው ዘመነ ክረምት የክርስትና ምሳሌ ሲኾን፣ ገበሬ በክረምት ብርዱንና ዝናሙን ሳይሰቀቅ ለሥራ ይሰማራል፤ በበጋው የእጁን ፍሬ ያገኝ ዘንድ የክረምቱን መከራ ይታገሣል፡፡ ይህም ምእመናን በሰማያዊው ዓለም የምናገኘውን ተድላና ደስታ በማሰብ በምድር ቆይታችን ወቅት የሚደርስብንን ልዩ ልዩ መከራ በትዕግሥት ማሳለፍ እንደሚገባን ያስገነዝባል፡፡

ዘመነ ክረምት ዕፀዋቱ በስብሰው ከበቀሉ፣ ካበቡና ካፈሩ በኋላ የሚጠቅሙት በጎተራ እንደሚሰበሰቡ፤ እንክርዳዶቹ ደግሞ በእሳት እንደሚቃጠሉ ኹሉ እኛም ተወልደን፣ አድገን፣ ዘራችንን ተክተን እንደምንኖር፤ ዕድሜያችን ሲያበቃም እንደምንሞት፤ ሞተንም እንደምንነሣና መልካም ሥራ ከሠራን ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እንደምንገባ፤ በኀጢአት ከኖርን ደግሞ በገሃነመ እሳት እንደምንጣል የምንማርበት ወቅት ነው፡፡

በመኾኑም ሰይጣን በሚያዘንበው የኀጢአት ማዕበል እንዳንወሰድና በኋላም በጥልቁ የእሳት ባሕር እንዳንጣል ኹላችንም ቅዱሳት መጻሕፍትና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያዘጋጁልንን የቃለ እግዚአብሔር ዘር በየልቡናችን በመጻፍ እንደየዓቅማችን አብበን፣ ያማረ ፍሬ አፍርተን መንግሥቱን ለመውረስ መዘጋጀት ይኖርብናል፡፡ ይህንን እንድናደርግም የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእናታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነትና የቅዱሳኑ ኹሉ ተራዳኢነት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ሕንጸተ ቤተ ክርስቲያን

በዝግጅት ክፍሉ

ሰኔ ፳ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በመጽሐፈ ስንክሳር እንደ ተመዘገበልን ሰኔ ፳ ቀን በኬልቄዶን አውራጃ በቂሣርያ አገር የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ያለ እንጨት፣ ያለ ጭቃና ያለ ውኀ በሦስት ድንጋዮች በተወደደ ልጇ በጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የታነጸበት ዕለት ነው፡፡ ይህ ዕለት በቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ ከሚከብሩ ከእመቤታችን በዓላት አንደኛው ሲኾን ታሪኩንም በአጭሩ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

ጌታችን በዐረገ በስምንተኛው ዓመት ቅዱስ ጳውሎስና ቅዱስ በርናባስ ወደ ፊልጵስዩስ ገብተው በክርስቶስ ስም አሳምነው ብዙ አሕዛብን ካጠመቁ በኋላ ቤተ ክርስቲያን ሊሠሩላቸው ወደዱ፡፡ በዚህ ጊዜ ርእሰ ሐዋርያት እያለ እኛ መሥራት አይገባንም ብለው በሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ መልእክት ላኩበት፡፡ እርሱም ከቅዱስ ዮሐንስ ጋር መጥቶ ከቅዱስ ጳውሎስ እና ቅዱስ በርናባስ ጋር በኢየሩሳሌም ተገናኙ፡፡

በዚያም በአንድነት ሱባዔ ይዘው ከቆዩ በኋላ ጌታችን የሞቱትን አስነሥቶ፣ ያሉትንም ጠርቶ ቅዱሳን ሐዋርያትን በፊልጵስዩስ አገር ሰብስቦ ‹‹በእናቴ በድንግል ማርያም ስም ከጽንፍ እስከ ጽንፍ የሚሠራዉን የአብያተ ክርስቲያናት ሥራ ላሳያችሁ፤ ሥርዓቱንም ላስተምራችሁ ሰብስቤአችኋለሁ›› ብሎ ወደ ምሥራቅ ይዟቸው ወጣ፡፡ በዚያ ሥፍራ የነበሩትን ሦስት ድንጋዮችንም የተራራቁትን አቀራርቦ፣ ጥቃቅኑን ታላላቅ አድርጎ ቁመቱን በ፳፬፤ ወርዱን በ፲፪ ክንድ ለክቶ ለቅዱሳን ሐዋርያት ሰጣቸው፡፡

ከዚህ በኋላ ቅዱሳን ሐዋርያት ሰም እሳት ሲያገኘው እንዲለመልም፣ ድንጋዩ በእጃቸው ላይ እየተሳበላቸው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑን ሠርተው ፈጽመዉታል፡፡ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ የተሠራዉም ጌታችን በዐረገ በ፲፱ኛው፤ እመቤታችን በዐረገች በ፬ኛው ዓመት ሰኔ ፳ ቀን ሲኾን፣ በ፳፩ኛው ቀን (በማግሥቱ) ኅብስት ሰማያዊ፣ ጽዋዕ ሰማያዊ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ወረደ፡፡ ጌታችንም ከእመቤታችን ጋር ከሰማየ ሰማያት መጥቶ እመቤታችንን ታቦት፤ ሐዋርያትን ልዑካን አድርጎ፣ እርሱ ሠራዒ ካህን ኾኖ ቀድሶ ካቈረባቸው በኋላ ‹‹እምይእዜሰ አንትሙኒ ከመዝ ግበሩ፤ ከዛሬ ጀምሮ እናንተም እንደዚህ አድርጉ›› ብሎ አዝዟቸው በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐርጓል፡፡

ይህ ታሪክ ብዙ ምሳሌዎች አሉት፡፡ ይኸውም፡- የሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ቁመት በነገሥታት ዘመን የነበሩ የ፳፬ቱ ነቢያት፤ አንድም የ፳፬ቱ ካህናተ ሰማይ አምሳል ሲኾን፣ ወርዱ ደግሞ የ፲፪ቱ ሐዋርያት ምሳሌ ነው፡፡ ሦስቱ ድንጋዮች የሥላሴ አምሳል ሲኾኑ፣ ከታች አቀማመጣቸው ሦስት፤ ከላይ ሕንጻቸው አንድ መኾኑ የሥላሴን ሦስትነትና አንድነት ያመለክታል፡፡ የሠሩትም ሦስት ክፍል አድርገው ሲኾን፣ ይህም የመጀመሪያው የታቦተ አዳም፤ ሁለተኛው የታቦተ ሙሴ፤ ሦስተኛው የታቦተ ኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ ዳግመኛም የሦስቱ ዓለማት ማለትም የመጀመሪያው የጽርሐ አርያም፣ ሁለተኛው የኢዮር፣ ሦስተኛው የጠፈር ምሳሌ ነው፡፡

አንድም መጀመሪያው የኤረር፣ ሁለተኛው የራማ፣ ሦስተኛው የኢዮር አምሳል ነው፡፡ በኤረር፡- መላእክት፣ መኳንንት፣ ሊቃናት፤ በራማ፡- ሥልጣናት፣ መናብርት፣ አርባብ፤ በኢዮር፡- ኃይላት፣ ኪሩቤል፣ ሱራፌል ይኖራሉ፡፡ እነዚህ ዘጠኙ ነገደ መላእክት የዘጠኙ መዓርጋተ ቤተ ክርስቲያን (መዓርጋተ ክህነት) አምሳል ሲኾኑ፣ ይኸውም መላእክት – የመዘምራን፤ መኳንንት – የአናጕንስጢሳውያን፤ ሊቃናት – የንፍቀ ዲያቆናት፤ ሥልጣናት – የዲያቆናት፤ መናብርት – የቀሳውስት፤ አርባብ – የቆሞሳት፤ ኃይላት – የኤጲስ ቆጶሳት፤ ሱራፌል – የጳጳሳት፤ ኪሩቤል – የሊቃነ ጳጳሳት አምሳሎች ናቸው፡፡

ይህም በታች (በምድር) የሚኖሩ ደቂቀ አዳም ከቅዱሳን በቀር ወደ ላይ (ወደ ሰማይ) መውጣት እንደማይቻላቸው፣ ከመዘምራን እስከ ጳጳሳት ድረስ ያሉ ካህናትም ከእነርሱ በላይ ያሉትን መዓርግ መሥራት (መፈጸም) እንደማይቻላቸው ያጠይቃል፡፡ እንደዚሁም በላይ የሚኖሩ መላእክት ወደ ታች መውረድ እንደሚቻላቸው ሊቃነ ጳጳሳትም ከእነርሱ በታች ያሉ ካህናትን ተልእኮ መፈጸም (መሥራት) እንደሚቻላቸው ያስረዳል፡፡

በጽርሐ አርያም መንበረ ብርሃን (የብርሃን መንበር)፤ ታቦተ ብርሃን (የብርሃን ታቦት)፤ መንጦላዕተ ብርሃን (የብርሃን መጋረጃ)፤ እንደዚሁም ፬ ፀወርተ መንበር (መንበሩን የሚሸከሙ)፤ ፳፬ አጠንተ መንበር (መንበሩን የሚያጥኑ) መላእክት አሉ፡፡ ጽርሐ አርያም – የመቅደስ፤ መንበረ ብርሃን – የመንበር፤ መንጦላዕተ ብርሃን – የቤተ መቅደሱ መጋረጃ፤ ፬ቱ ፀወርተ መንበር – የ፬ቱ ሊቃነ ጳጳሳት ወይም የመንበሩ እግሮች፤ ፳፬ቱ አጠንተ መንበር – የጳጳሳት (የኤጲስ ቆጶሳት) አምሳሎች ናቸው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡-

  • መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሰኔ ፳ ቀን፡፡
  • መጽሐፈ ታሪክ ወግስ፣ መ/ር አፈወርቅ ተክሌ፤ አዲስ አበባ፣ ፳፻፭ ዓ.ም፤ ገጽ ፫፻፵፱ – ፫፻፶፩፡፡

አባ ገሪማ ዘመደራ

ሰኔ ፲፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲቆን ኤፍሬም የኔሰው

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ እንደሚነግረን በጉባኤ ኤፌሶን የተወገዘውን፣ በኋላም በጉባኤ ኬልቄዶን ጊዜ በመለካውያን አማካኝነት የመጣውን የሁለት አካል፣ ሁለት ባሕርይ የኑፋቄ እምነት አንቀበልም በማለታቸው በባዛንታይን ነገሥታት ስቃይ የጸናባቸው ተስዓቱ (ዘጠኙ) ቅዱሳን መነኮሳት ከሶርያና ከታናሽ እስያ ተሰደው በአልአሜዳ ዘመነ መንግሥት በ፬፻፹ ዓ.ም ወደ አገራችን ወደ ኢትዮጵያ መጥተዋል፡፡

በዘመኑ የነበረው የኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥትም ከአባቶቹ በወረሰው የደግነትና እንግዳ ተቀባይነት ባህሉ በፍቅር ተቀብሏቸዋል፡፡

እነዚህ ዘጠኙ ቅዱሳን በመላው ኢትዮጵያ ተዘዋውረው ወንጌልን ሰብከዋል፤ በወቅቱ ብሔራዊ ቋንቋ የነበረዉን ግእዝ በሚገባ አጥንተው ቅዱሳት መጻሕፍትን ከሱርስትና ከጽርዕ ቋንቋዎች ወደ ግእዝ ተርጕመዋል፡፡ እንደዚሁም በስማቸው የሚጠሩ ገዳማትንና ሌሎችንም አብያተ ክርስቲያናት አሳንፀዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችንም ከፈጸሟቸው መንፈሳውያን ተልእኮዎች፣ ካደረጓቸው ተአምራትና መልካም ሥራዎች አኳያ ቅዱሳን በሚል መዓርግ ትጠራቸዋለች፤ በስማቸውም ጽላት ቀርፃ በዓላቸውን ታከብርላቸዋለች፡፡

ዘጠኙ ቅዱሳን የሚባሉት አባቶችም፡- አባ አሌፍ፣ አባ አረጋዊ፣ አባ አፍጼ፣ አባ ሊቃኖስ፣ አባ ገሪማ፣ አባ ጉባ፣ አባ ይምአታ፣ አባ ጰንጠሌዎን እና አባ ጽሕማ ናቸው፡፡ /ምንጭ፡- የኢ.ኦ.ተ.ቤ.ክ.ታ፣ አባ ጎርጎርዮስ ዘሸዋ፣ ፲፱፻፺፩ ዓ.ም፤ ገጽ ፳፫-፳፬/፡፡

በዛሬው ዝግጅታችን ከዘጠኙ ቅዱሳን አንዱ የኾኑትን የአባ ገሪማን ታሪክ በአጭሩ እናስታውሳችኋለን፤

በሮም አገር መስፍንያኖስ የሚባል ንጉሥ ነበረ፤ ሚስቱም ሰፍንግያ ትባላለች፡፡ መካን ስለነበረች በቅድስት ድንግል ማርያም ስም በመማጸን ልጅ እንዲሰጣት እግዚአብሔርን ስትለምን ከኖረች በኋላ ወንድ ልጅ ወለደች፤ ስሙንም ይስሐቅ አለችው፡፡ የያን ጊዜው ይስሐቅ የኋላው አባ ገሪማ በመንፈሳዊ ሥርዓት ካደገ በኋላም የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ተምሮ በዲቁና ማገልገል ጀመረ፡፡

ይስሐቅ ወላጅ አባቱ ሲሞትም በአባቱ ዙፋን ተተክቶ ለሰባት ዓመታት ሮምን በንጉሥነት ሲያስተዳድር ከቆየ በኋላ በዋሻ ይኖሩ የነበሩት አባ ጰንጠሌዎን ዘጾማዕት *ይስሐቅ ሆይ፣ ሙታኖቻቸውን ይቀብሩ ዘንድ ሙታንን ተዋቸውና የማያልፈዉን የክርስቶስን መንግሥት ትሻ ዘንድ ወደ እኔ ና፤* ብለው ላኩበት፡፡ መልእክቱ እንደ ደረሰውም መንግሥቱን ትቶ በሌሊት ወደ አባ ጰንጠሌዎን ሲሔድ ቅዱስ ገብርኤል ተገልጾ በብርሃናውያን ክንፎቹ ተሸክሞ ዐሥር ወር የሚወስደዉን መንገድ በሦስት ሰዓታት አስጉዞ ከአባ ጰንጠሌዎን ደጅ አደረሰው፡፡

አባ ይስሐቅ (አባ ገሪማ) በአባ ጰንጠሌዎን እጅ ከመነኰሱ በኋላ በጾም፣ በጸሎትና በስግደት ተጠምደው ቆዳቸው ከዐፅማቸው እስኪጣበቅ ድረስ ተጋድሎ ሲፈጸሙ ከቆዩ በኋላ ወደ መደራ ሔደው በእግዚአብሔር ኃይል ድንቆችንና ተአምራትን እየያደረጉ፣ በሽተኞችን እየፈወሱ፣ አጋንንትን እያስወጡ ብዙ ዘመን ኖሩ፡፡

ካደረጓቸው ተአምራት መካከልም በጠዋት ሥንዴ ዘርተው፣ በሠርክ ሰብስበው መሥዋዕት ካሳረጉ በኋላ በማግሥቱ ከግራር ዛፍ ላይ በሬዎችን አውጥተው ሥንዴዉን አበራይተው ሰባ ሰባት የእንቅብ መሥፈሪያ መሰብሰባቸው አንደኛው ሲኾን፣ ዳግመኛም በዓለት የተከሏት ወይን ወዲያው በቅላ፣ አብባ አፍርታለች፤ በዚህም መሥዋዕት አሳርገዋል፡፡

እንደዚሁም አንድ ቀን መጽሐፍ እየጻፉ ሳሉ ፀሐይ ሊጠልቅ በተቃረበ ጊዜ ጸሎት አድርሰው ጽሕፈታቸዉን እስኪፈጽሙ ድረስ እንደ ኢያሱ ፀሐይን በቦታው እንዲቆም አድርገዋል፡፡ ምራቃቸዉን ትፍ ያሉበት ሥፍራም እስከ ዛሬ ድረስ ሕሙማን ይፈዉሳል፡፡ እንደዚሁም ከእጃቸው የወደቀው ብርዕ ወዲያው መብቀሉንና አቈጥቍጦ ማደጉን መጸሐፈ ስንክሳር ይናገራል፡፡

በአንዲት ዕለትም መቅኑናቸውን ተቀብለው ከመነኮሳት ጋር ሲሔዱ መንገድ ላይ ቤተ ክርስቲያን አግኝተው ሲጸልዩ ካህናቱ ቅዳሴ እንዲያሟሉላቸው በጠየቋቸው ጊዜ ሌሎቹ ምግብ በልተው ነበርና አንችልም ሲሉ አባ ይስሐቅ ግን ምግብ አልተመገቡም ነበርና መቅኑናቸዉን አስቀምጠው ቅዳሴውን አሟልተዋል፡፡ ባልንጀሮቻቸው ግን በልተው የቀደሱ መስሏቸው ወደ አባ ጰንጠሌዎን መጥተው *ቀሲስ ይስሐቅ ከበላ በኋላ ቀደሰ* ብለው ከሰሷቸው፡፡

አባ ጰንጠሌዎንም አባ ይስሐቅ ሲመለስ *የምጠይቅህ ምሥጢር ስላለኝ ሰዎችን ከአጠገብህ ገለል አድርጋቸው* ሲሏቸው አባ ይስሐቅም *ሰዎች ብቻ ሳይኾኑ ዕንጨቶችና ድንጋዮችም ገለል ይበሉ* ብለው መለሱላቸው፡፡ ወዲያዉኑም ዕንጨቶችና ድንጋዮች አንድ ምዕራፍ ያህል ከቦታቸው ሸሹ፡፡

በዚህ ጊዜ አባ ጰንጠሌዎን *ኦ ወልድየ ይስሐቅ ገረምከኒ፤ ልጄ ይስሐቅ ገረምከኝ* ሲሉ አደነቋቸው፡፡ አባ ገሪማ ተብለው መጠራት የጀመሩትም ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ነው፡፡ ይህንን መሠረት በማድረግ ቅዱስ ያሬድ በመዝሙሩ *ገሪማ ገረምከኒ አስኬማከኒ አልባቲ ሙስና፤ አባ ገሪማ አስገረምኸኝ፡፡ ለምንኵስናህም እንከን የለባትም፤* በማለት አመስግኗቸዋል፡፡

አባ ገሪማን ሳያዉቁ የከሰሷቸው መነኮሳትም ይቅርታ ጠይቀዋቸዋል፡፡ ከዚያም መደራ ገብተው በዓት ሠርተው ለ፳፫ ዓመታት በትኅርምት ኖረው መልካም ተጋድሏቸውንና የቀና አካሔዳቸዉን በፈጸሙ ጊዜ ክብር ይግባውና ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰኔ ፲፯ ቀን ተገልጦ ስማቸውን የሚጠሩትን፣ መታሰቢያቸዉን የሚያደርጉትን፣ ገድላቸዉን የሚጽፉ፣ የሚያነቡና የሚተረጕሙትን፣ ቤተ ክርስቲያን የሚያንፁትንና የሚያገለግሉትን ስማቸውን በሕይወት መጽሐፍ እንደሚጽፍላቸው ቃል ኪዳን ሰጥቷቸዋል፡፡

አባ ገሪማም ይህንን ታላቅ ሀብት የሰጣቸዉን እግዚአብሔርን አመስግነው ከተደሰቱ በኋላ በብርሃን ሠረገላ ተነጥቀው ብሔረ ሕያዋን ገብተዋል፡፡ አባ ገሪማ የተሠወሩበት ሰኔ ፲፯ ቀን በቤተ ክርስቲያናችን በተለይ በገዳማቸው በመደራ በየዓመቱ በድምቀት ይከበራል፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይኹን፡፡ እኛንም በጻድቁ ጸሎት ይማረን፤ በረከታቸዉም ከእኛ ጋር ትኑር፤ ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

ምንጭ፡-

መጽሐፈ ስንክሳር፣ ሰኔ ፲፯ ቀን፡፡

መዝገበ ታሪክ ክፍል ፪፣ መ/ር ኅሩይ ኤርምያስ፣ ገጽ ፺፱-፻፡፡