hammer site Home .JPG

ለሐመር መጽሔት መካነ ድር /website/ ተሠራለት፡፡

ለ18 ዓመታት ትምህርተ ሃይማኖታዊ ክርስቲያናዊ ሕይወትን፣ ማኅበራዊ ኑሮንና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን ምዕመኑን ስታስተምር የዘለቀችው ሐመር መጽሔት ለራሷ የሚያገለግል መካነ ድር ተዘጋጀላት፡፡የመካነ ድሩም አድራሻ(URL) http://hamer.eotc-mkidusan.org ነው።

በቀደመው ጊዜ ብዙ የተደከመባቸውና ዋጋ የተከፈለባቸው የኅትመት ውጤቶች ምዕመናን እንዲጠቀሙበት ታስቦ እንደተሠራ በማኅበረ ቅዱሳን የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ሓላፊ ዲ/ን ዘላለም ቻላቸው ተናግረዋል፡፡

ለወደፊቱም የሚወጡትን የመጽሔቷን ዝግጅቶች በሽፋን /cover/ ገጽ በማስተዋወቅ ሥርጭቷን ከፍ የማድረግና በዚህም ስብከተ ወንጌልን የማስፋፋት ተልዕኮን የበለጠ ማሳለጥን ዓላማ ያደረገ እንደሆነ የገለጹት ዲ/ን ዘላለም ቤተ ክርስቲያን በየዘመናቱ የጽሕፈትና የመገናኛ ቴክኖሎጂውን በቀዳሚነት ስትጠቀም ቆይታለች፡፡ አሁን ደግሞ የሰዎች ኢንተርኔትን የመጠቀም እውነታ ቤተ ክርስቲያንን ተወዳዳሪ ሊያደርጋት ይገባል በማለት አያይዘው አስረድተዋል፡፡ 1985 content preview.JPG

በአንዳንድ አቻ መካነ ድሮች ከጥንት አባቶች እስከ ቅርብ ጊዜ ያሉት ጽሑፎችና ሥራዎችን ማግኘት ይቻላል፡፡ በአገራችንም አንዳንድ የኅትመት ውጤቶች የቀጥታ የኢንተርኔት/Online Journalism/ ዘገባ እየጀመሩ እንደሆነ ሌሎችም የቆዩ ሕትመቶቻቸውን የሚያስነብቡበት መካነ ድር እንዳላቸው ይታወቃል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት ቅድሚያ እንደሚሰጥ የሚገልጹት ዲ/ን ዘላለም በብዙ ሀገሮች መድረስ የሚችል መካነ ድር በአሁኑ ጊዜ ተመራጭ ሚዲያ እንደሆነ ነው፡፡

ለወደፊቱም ለስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ ለጥናትና ምርምር ማእከል፣ ለቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት እንዲሁም ለሌሎች ዋና ክፍሎች ድረ ገጾችን የመሥራት ሐሳብ እንዳለ ሓላፊው አስታውቀዋል፡፡

መካነ ድሩን ያዘጋጁት አቶ ደመላሽ ጋሻው በኤሌክትሮኒክስ ሚድያ ክፍል የቴክኖሎጂ ንዑስ ክፍል አባል ሲሆኑ በዚህ ወቅት መካነ ድሩ ከ45 እትሞች የሚበልጡ ከ1985 እስከ 2001 ዓ.ም የሚገኙ እትሞችን /ከጠቅላላው እትም ከ45-50% የሚሆን /እንዳካተተ ተናግረዋል፡፡ በሰው ኃይል እጥረት፣ በአንዳንድ እትሞች አለመገኘት ወይም ተጠርዘው መቀመጣቸው ስካን /Scan/ ለማድረግ አለመመቸቱ ሁሉንም የቀድሞ እትም መልቀቅ አልተቻለም በማለት አስረድተዋል፡፡ያልተሟሉ ቀሪ ሕትመቶችም በየጊዜው ስካን እየተደረጉ እንደሚጨመሩ አክለው ገልጸዋል።

መካነ ድሩ በአሁኑ ጊዜ ለመጠቀም ምቹና ቀላል ሲሆን እትሞቹንም በዓመት ማግኘት ይቻላል፡፡ በተጨማሪም ምን እንደተለወጠ የሚገልጽ አካል አካቷል፡፡ ለወደፊትም የሕትመት ውጤቶችን በደራሲ፣ በእትም ቁጥር፣ በውስጡ ይዘት /content/፣ የመጽሔቱን ዓምዶች መሠረት ባደረገ ክፍፍል የፍለጋ /Search/ ሥርዓትን ያካትታል፡፡ ከዚህም በላይ የቀጥታ ሽያጭ /Online selling/ እና የቀጥታ ምዝገባ /Online Registration/ እንደ ቴክኖሎጂው ተጨባጭ ሁኔታ ይይዛል በማለት አቶ ደመላሽ አስታውቀዋል፡፡ 1985 no 1 content .JPG

መካነ ድሩን ለመስራት የሚያስፈልገው ወጪ ከ10,000-15,000 ብር የሚገመት ሲሆን ሥራውም ከዓመት በፊት እንደተጀመረ ታውቋል፡፡ ሐመር መጽሔት በ20ኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻና በ21ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ስብከተ ወንጌልን በማስፋፋት፣ በእቅበተ ቤተ ክርስቲያን /Apology/፣ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን እንዲጠበቅ በማሳሰብ /በማስተማር/ ታዋቂነት ያላት መጽሔት ናት።

መጽሔቷም በስርጭት ስፋትና በሽያጭ የመጀመሪያ ስትሆን ላለፉት ተከታታይ 18 ዓመታትም ያለ ማቋረጥ በማገልገል ታሪካዊ ናት፡፡

የመዝሙር ዐውደ ርዕይ ተከፈተ

  በዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ 
ሰኔ 29፣ 2003 ዓ.ም
 
ማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማዕከል ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት የመዝሙር ንዑስ ክፍል የተዘጋጀ የመዝሙር ዐውደ ርዕይ ሰኔ 28/2003 ዓ.ም በሊቀ ትጉኃን ቀሲስ ዶክተር ሙሉጌታ ስዩም እና በመዝገበ ጥበባት ጌትነት በማኅበረ ቅዱሳን ሕንጻ ላይ ተከፈተ፡፡  
 
የመዝሙሩ ዐውደ ርዕይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ጸዋትወ ዜማ፤ የዜማ ይትበሃል፤ የዜማ (የመዝሙር) መሣሪያዎችና ምሥጢራዊ ምሳሌነታቸውን፤ የአማርኛ መዝሙራት እንዲሁም ማኅበረ ቅዱሳን በመዝሙር ዙርያ ያከናወናቸው ተግባራትን ያስቃኛል፡፡
በመጀመሪያው ትዕይንት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ጸዋትወ ዜማ በሚል÷ በውስጡ የቅዱስ ያሬድን የዜማ ስልት(ዓይነት)፤ የቅዱስ ያሬድን የዜማ ድርስቶች እና የዜማ ምልክቶች እንዲሁም ቅዱስ ያሬድ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ያደረገው አስተዋጽኦ የቀረበበት ነው፡፡ ሁለተኛው ትዕይንት በውስጡ ስለ የዜማ ይትበሃል፣ ምንነትና ታሪካዊ አመጣጥ ያስቃኛል፡፡ የሦስተኛው ትዕይንት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የዜማ (የመዝሙር) መሣሪያዎችና ምስጢራዊ ምሳሌነታቸውን የሚቀርብበት ነው፡፡ አራተኛው ትዕይንት ስለ አማርኛ መዝሙር ምንነትን ፣ የመዝሙር ጥቅምን ፣ የአማርኛ መዝሙር አጀማመርና መስፈርቶች ፣ አሁን ያለበት ሁኔታ እና መዝሙርን ሁሉ እንዳገኘን ብንዘምር ምን ችግር ያስከትላል የሚሉ ንዑሳን ርዕሶች ተካተዋል፡፡ የመጨረሻው ትዕይንት ማኅበረ ቅዱሳን በመዝሙር ዙርያ ያከናወናቸውን ተግባራት ያስቃኛል፡፡

ዐውደ ርዕዩ አባቶቻችን ያቆዩልንን የቤተ ክርስቲያን አሻራ የሆነውን ዜማችንን የሚያሳውቅ፣ የሰንበት ት/ቤቶች መዝሙር አሁን ያለበትን ደረጃ የሚያሳይ እንዲሁም በመዝሙር ዙሪያ ላሉ ችግሮች የመፍትሔ ሐሳብ የሚወሰድበት ነው፡፡

በዕለቱ አንዳንድ እንግዶች አስተያየት የሰጡ ሲሆን ከነዚህ መሀል መዝገበ ጥበባት ጌትነት እንዳሉት ‹‹ያየሁት ለሰሚ ድንቅ ነው፡፡ ብዙዎች ቢያዩት መልካም ነው›› ሲሉ ሊቀ መዘምራን ኪነጥበብ ወልደ ቂርቆስ በበኩላቸው ‹‹ያለው የነበረው የቀረበበት›› ዐውደ ርዕይ ነው ብለዋል፡፡

 
ከዝግጅቱ አስተባባሪ ወ/ት ገነት አባተ እንደተረዳነው ዝግጅቱ ከሰኔ 29/2003 ዓ.ም እስከ ሐምሌ 3/2003 ዓ.ም ከጠዋቱ 2፡30 እስከ ምሽቱ 2፡30 ለምዕመናን ክፍት ሆኖ የሚቆይ ሲሆን÷ በመዝጊያው ዕለት ሐምሌ 3/2003 ዓ.ም ከ7፡30 እስከ 11፡30 ለየት ያለ ዝግጅት እንደሚኖር ነግረውናል ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በመዝሙር ዙሪያ ዐውደ ርዕይ ሲያዘጋጅ ይህ የመጀመሪያው ነው፡፡
                                                           

የወልደ ነጎድጓድ ልጆች እንቅስቃሴ

በፈትለወርቅ ደስታ
 ሰኔ 28ቀን 2003ዓ.ም

 

ጊዜው ትውልዱ በሶሻሊዝም ፍልስፍና እየተሳበ የነበረበት ነበር፡፡ 1960ዓ.ም ማለትም የዛሬ 43 ዓመት ሆነ፡፡ የቤተ ክርስቲያኗ አስተዳደር የነበሩት መምህር መዘምርና መምህር ዘውዴ የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ ሰንበት ትምህርት ቤትን እንደመሠረቱት የሚነገረው በዚህ ጊዜ ነው፡፡ ሕፃናትንና ወጣቶችን በመሰብሰብ ምሥረታው አሐዱ የተባለው ሰንበት ትምህርት ቤት አሁን በሕይወት የሌሉት ብፁዕ አቡነ ያዕቆብ የቅርብ ክትትል ይደረግለት ነበር፡፡ ብፁዕነታቸው የደብሩ አስተዳዳሪ በነበሩበት ወቅት አባላትን እንደልጅ እየኮተኮቱና እየተንከባከቡ ያሳድጓቸው ነበር፡፡ ቅዳሜና እሑድ የሚሰጠውን የትምህርት መርሐ ግብር የሚመጡትንም /የሚመደቡትን/ መምህራንና የሚያስተምሩትን ትምህርት በመቆጣጠርና በማረም ሰንበት ትምህርት ቤቱን ጥሩ ደረጃ ላይ አድርሰውታል፡፡

የትምህርት መርሐ ግብር

ሥርዓተ ትምህርት በመቅረጽ ለምዕመናን ጥሪ በማድረግ የሚያስተምረው ሰንበት ትምህርት ቤቱ በዓመት ሁለት መርሐ ግብሮች አሉት፣ በበጋና በክረምት የሚከናወኑ፡፡ ከሰኞ እስከ አርብ በማታው መርሐ ግብር እንዲሁም ቅዳሜና እሑድ ደግሞ በቀን መርሐ ግብር ለምእመናን የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ያስተምራል፡፡ የተማሪዎችንም የክረምት እረፍት ተከትሎ ተጠናክሮ ይካሄዳል፡፡

በእድሜ ክልል በመክፈል ቀዳማይ፣ ካልዓይና ሣልሳይ በማለት የአንድ ዓመት ኮርሶችን ያስተምራል፡፡ ትምህርተ ሃይማኖት፣ ክርቲያናዊ ሥነ ምግባር፣ ታሪክ በመጽሐፍ ቅዱስ፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ለዓለም መድረክና በኢትዮጵያ፣ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን እንዲሁም የዮሐንስ ወንጌል አንድምታ ከሚሰጡት ውስጥ ይጠቀሳሉ፡፡

ከጥሩ ተሞክሮዎቹ

ይህን ያህል የገነነ ተሞክሮ የለንም በማለት በትሕትና የሚገልጡት የሰንበት ትምህርት ቤቱ ሰብሳቢ አቶ አበበ ሥዩም ጥቂቶቹን ይገልጻሉ፡፡

ከአዲስ አበባ ወጣ ካሉ ሰንበት ትምህርት ቤት ጋር ጥሩ ግንኙነት እንደመሠረቱ የሚገልጡት አቶ አበበ ኪናዊ የሆነ ሥራዎችን በማዋስ፣ ልምድ ለማካፈል እንደሚያግዟቸው ይናገራሉ፡፡

በነሐሴ 16 እና የካቲት 16 ዓመታዊ የኪዳነ ምሕረት በዓላት ወደ ፍቼ ኪዳነ ምሕረት በመጓዝ ሙሉ መርሐ ግብር በመሸፈን አገልግሎት ይሰጣል፡፡ ነገር ግን አሁን አሁን ቀዝቀዝ በማለቱ ለማጠናከር ጥረት እየተደረገ ነው ይላሉ ሰብሳቢው፡፡

በቤተ ክርስቲያንና በሰንበት ትምህርት ቤቱ ላይ ፈተና ሲመጣ መባ ይዞ በመሄድ ወይም በመላክ በጸሎት እንዲያስቡ ያደርጋሉ ሰንበት ትምህርት ቤቱ በራሱም የጸሎትና የጉባኤ መርሐ ግብር በማዘጋጀት በቂ ግንዛቤ ያስጨብጣል፡፡ አብዛኛው ምእመን ሱባኤ በመያዝ በየገዳማቱና የገጠር አብያተ ክርስቲያናት በሚያሳልፍበት በጳጉሜን ወር ትምህርት ጸሎትና ምክረ አበው በማዘጋጀት እንዲያሳልፍ ያደርጋል፡፡ ይሄም የሚናፈቅ እንደሆነ የሰንበት ትምህርት ቤቱ አባላት ይገልጻሉ፡፡

የአብነት ትምህርትን በማስተማር በኩል ሊጠቀስ የሚችል ሥራ ሠርቷል፣ ሰንበት ትምህርት ቤቱ እንደ ዲያቆን ወሳኙ ገለጻ ሰንበት ትምህርት ቤቱ የአብነት ትምህርት ማስተማር ከጀመረ ወደ ሰባት ዓመት አስቶጥሯል፡፡ በእነዚህ ጊዜያት ወደ 20 የሚጠጉ ዲያቆናት አፍርቷል፡፡ በአሁኑ ጊዜ በደብሩም ውስጥ የሚያገለግሉ አሉ፡፡ ቢሆንም የሚጠበቅበትን ያህል እየሄደ እንዳልሆነ የሚገልጹት ዲያቆን ወሳኙ ከዚህ በፊት የነበሩት አንድ መምህር ብቻ መሆናቸውና እርሳቸውም ደጅ ጠኚ ሆነው በትራንስፖርት /በመጓጓዣ/ አበል ብቻ ያስተምሩ እንደነበር ነው፡፡ ትምህርቱም ሥርዓተ ትምህርት ተቀርጾለት አለመሰጠቱ ሌላው ችግር ነው፡፡ ይህም የተፈለገውን ያህል ለማስፋፋት እንዳላስቻለ ይገልጻሉ ዲ/ን ወሳኙ፡፡

ሰንበት ትምህርት ቤቱ ለአብነት ትምህርቱ ምእመናን እንዲሳተፉ ቅስቀሳ የሚካሄደው የደብረ ታቦር ዕለት ነው፡፡ የቆሎ ትምህርት ቤትን ገጽታ የሚያሳይ ኪናዊ ሥራ በማሳየት አውደ ምሕረት ላይ ቅስቀሳ ይደረጋል፡፡ ምንም እንኳን በርካታ ወጣቶች ቢመዘገቡም፤ ጥቂቶች ብቻ ለውጤት እንደሚበቁ ይገልጻሉ ዲ/ን ወሳኙ፡፡ አሁን ግን ቤተ ክርስቲያኗ የአብነት መምህር በመቅጠሯ የተሻለ የመማር እድል አለ፡፡

የወደፊት እቅድ

በጅምር ላይ ያለው የሰንበት ትምህርት ቤቱ አዳራሽ ሲያልቅ በውስጡ የእደ ጥበብ ሥራዎችን በማምረት ያከፋፍላል፣ ይሸጣል፣ ከሌሎች ሰንበት ትምህርት ቤቶችና ማኅበራት ጋር በመቀናጀት ሙያዊ ሥልጠናዎችን፣ ተሞክሮዎችንና ድጋፍ ካገኘ በኋላ የልማት ሥራዎችን ይሠራል፡፡

በመጪዎቹ አሥር ዓመታት ውስጥ የአብነት ትምህርት ቤቱን በማጠናከር አብነት መር የሆነ ሰንበት ትምህርት ቤት ለመፍጠር እቅድ አለ፡፡ ይህንንም ለመፈጸም ጥናቱን አጠናቆ ተግባራዊ ይደረጋል ብለዋል ዲ/ን ወሳኙ፡፡

ሁሉም ሰንበት ትምህርት ቤቶች እጅ ለእጅ ተያይዘን አንዲት ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ቆርጠን መነሣት አለብን በማለት የሚያሳስቡት የሰንበት ትምህርት ቤቱ አቶ አበበ ስዩም በአሁኑ ጊዜ ቤተ ክርስቲያን የገጠማትን ከበድ ያለ ወቅታዊ ፈተና ያነሣሉ፡፡

“ቤተ ክርስቲያን እውነት በመያዟ ልትፈተን የግድ ነው፡፡ ነገር ግን የተፈጠረባትን ፈተና እንዲጋፈጡ ለተወሰኑ ሊቃነ ጳጳሳት፣ መምህራንና ማኅበራትና ሰንበት ትምህርት ቤቶች የመተው ሁኔታ አለ፡፡ ይሄ ደግሞ ፈተናውን የከፋ እንዲሆን ያደርገዋል፡፡” በማለት ዲ/ን ወሳኙ ያክላሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያንን እኛ የምንታደጋት የሚቀርባት ስላለ ሳይሆን እኛ የሚቀርብን ስላለ ነው፡፡ የድርሻችንን አውቀን መወጣት እንጂ የእነ እገሌ ብሎ ለሌላ መስጠት ተገቢ አይደለም በማለት ያሳስባሉ፡፡

በቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ምድር ቤት ፊት ለፊት ደረጃው ሥር ባሉ ክፍሎች በመሰባሰብ የተጀመረው ሰንበት ትምህርት ቤቱ፣ ቀጥሎም በክርስትና ቤት፤ የአባላት ቁጥር ሲጨምርም ትልቅ የቆርቆሮ ቤት በመሥራት እንዲቀጥል ሆኗል፡፡ በእግዚአብሔር ፈቃድ የያኔው ተክል እያበበ እያፈራ 43 ዓመቱን ያከበረው ባለፈው ከግንቦት 19 እስከ 21 ቀን 2003 ዓ.ም ለሦስት ቀናት በተዘጋጀ መርሐ ግብር ነበር፡፡ የሰንበት ትምህርት ቤቱ የኪነ ጥበብ ክፍል ከላሊበላ አርቲስቶች ጋር በመተባበር “ተዋሕዶ” በሚል ርዕስ ያዘጋጁትን ድራማ ለምእመናን አቅርበዋል፡፡ በሦስቱ ቀን መርሐ ግብር የልማትና የጸሎት ክፍል የጸሎት መርሐ ግብር አዘጋጅቶ ነበር፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ጉዳይና አጽራረ ቤተ ክርስቲያንን በተመለከተም በጉባኤው ላይ ለታደሙት ምእመናንና ተጋባዥ እንግዶች መረጃ እንደደረሰ ዲ/ን ወሳኙ ዘውዴና አቶ አበበ ስዩም ገልጸዋል፡፡

“የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሚና በአየር ንብረት ለውጥ” በሚል መሪ ቃል ጥናታዊ የውይይት መድረክ ተካሄደ

ዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ
 
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማዕከል “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሚና በአየር ንብረት ለውጥ“ በሚል መሪ ቃል ሰኔ 18 ቀን 2003 ዓ.ም በኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዝየም መሰብሰቢያ አዳራሽ ጥናታዊ የውይይት መድረክ ተካሄደ፡፡
 
በዕለቱ አምስት ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ ከነዚህም ጥናታዊ ጽሑፎች በጠዋቱ ክፍለ ጊዜ “የዓባይ ወንዝና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን” የሚል ጥናታዊ ጽሑፍ በአቶ ዘሪሁን አበበ ቀርቧል፡፡ አቶ ዘሪሁን በጥናታቸው በዋናነት የውኃ ፖለቲካ ከምሥራቅ አባይ ተፋሰስ/ናይል/ አንጻር፣ በዚህም መሠረት ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምን ዓይነት ቁርኝት አላት? የውሃው ፖለቲካ እንዴት ነው ተጽዕኖ ሊፈጥርባት የሚችለው? ምን ዓይነት የራሷ የሆነ ጥቅም አላት?  የሚለውን በማሳየት ሰፋ ያለ የጥናት ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

በመቀጠል በአቶ ወንድወሰን ሚቻጎ “የአየር ንብረት ለውጥና ሃይማኖታዊ እሳቤ” በሚል ጥናታዊ ጽሑፍ ቀርቧል፡፡ አቶ ወንድወሰን በጥናታቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶከስ ቤተ ክርስቲያን በአየር ለውጥ ላይ ምን ዓይነት ሚና አላት? ዕውቀት በአየር ንብረት ለውጥ ላይ ያለው አስተዋጽኦና የሃይማኖት እሳቤ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ አስተዋጽኦ የሚያመጣው ምንድን ነው? በሚል ሰፋ ያለ የጥናታዊ ጽሑፍ መነሻቸውን አቅርበው ጥያቄዎችና አስተያየቶች ከተሰጡ በኋላ የጠዋቱ ክፍለ ጊዜ ተጠናቋል፡፡

ከሰዓት በኋላ በነበረው ክፍለ ጊዜ ሦስት ጥናታዊ ጽሑፎች የቀረቡ ሲሆን በመጀመሪያው ክፍለ ጊዜ “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አስተዋጽኦ የካርቦን ልቀትን ለመከላከል “በሚል በዲያቆን ቱሉ ቶላ ቀርቧል፡፡ ዲያቆን ቱሉ በአዲስ አበባ በሚገኙ ሰባት ቀደምት አድባራትና ገዳማት ላይ ተመርኩዘው የሠሩትን ጥናት አቅርበዋል፤ በመቀጠል በአቶ ተስፋዬ አራጌ “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሚና ለተፈጥሮ ደን ጥበቃና እንክብካቤ” በሚል በደቡብ ጎንደር በሚገኝ ሦስት በተመረጡ ወረዳዎች ባሉ አስር አብያተ ክርስቲያናት ስለ ደንና አጠባበቅ የተደረገ ጥናት አቅርበዋል፣ በመጨረሻም በአቶ ብርሃኑ በላይ “የቅብዓ ሜሮን ዕፅዋት የዳሰሳ ጥናት” በሚል ጥናት፣ ሜሮንን ለማዘጋጀት የምንጠቀምባቸው ዕፅዋት እነማን ናቸው? በቀጣይስ እነዚህ ዕፅዋቶች እንዴት ነው? ማሳደግና መንከባከብ የምንችለው? በሚል መነሻ ጥናታቸውን አቅርበዋል፡፡

ከጥናታዊ ጽሑፎች ጋር ተያያዥነት ካላቸው ከአዲስ አባባ ዩኒቨርሲቲ፣ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ካልሆኑ ተቋማት እንዲሁም በግል የተጋበዙ ከ300 በላይ እንግዶች የተገኘበት ሲሆን፣ በመጨረሻም የጥናትና ምርምር ማዕከሉ አማካሪ፣ የሰቲት ሁመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ሉቃስ “ጊዜ ገቢር ለእግዚአብሔር” በሚል ርዕስ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ተሰጥቶ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማዕከል ከተመሠረተ ጀምሮ በርካታ ጥናታዊ የውይይት መድረኮችን ያካሄደ ሲሆን ባለፈው ዓመትም የመጀመሪያውን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት መጽሔት አሳትሞ አበርክቷል፡፡

ቀሲስ ለማ በሱፍቃድ

ማኅበረ ቅዱሳን 20ኛውን ሐዋርያዊ ጉዞ በሰሜን ምሥራቅ ኢትዮጵያ በተሳካ ሁኔታ አደረገ

በዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ

ሰኔ 20 ቀን 2003ዓ.ም

ማኅበረ ቅዱሳን በትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ከግንቦት 19 – ሰኔ 1 ቀን 2003 ዓ.ም ድረስ በሰሜን ወሎ እና ደቡብ ትግራይ አህጉረ ስብከቶች ሃያ ሰባት ልዑካንን በመያዝ ሐዋርያዊ ጉዞ ማድረጉን በትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል መደበኛ መምህርና የሐዋርያዊው ጉዞ አስተባባሪ ቀሲስ ለማ በሱ ፍቃድ አስታወቁ፡፡

ቀሲስ ለማ በሱፍቃድቀሲስ ለማ በሱ ፍቃድ እንዳሉት ሐዋረያዊ ጉዞው ከሁለት አህጉረ ስብከቶች በተመረጡ ሰባት ዋና ዋና ከተሞች ማለትም ከደቡብ ወሎ /መርሳ ወልዲያ፣ ፍላቂትና ቆቦ/ እንዲሁም ከደቡብ ትግራይ /አላማጣ፣ ኮረምና ማይጨው/ ማኅበሩ በእነዚህ ሁለት የተመረጡ አህጉረ ስብከቶች ሐዋርያዊ ጉዞ ያካሄደበትን ዓላማ ቀሲስ ለማ እንዲህ በማለት አብራርተዋል፤ ሕዝቡና ካህኑ እንዳለ ተከባብሮ የሚኖርበት ቦታ በመሆኑ፥ አህጉረ ስብከቶቹ የብዙ ሊቃውንት መፍለቂያ፣ የታላላቅ አድባራትና ገዳማት ባለቤት እንዲሁም ብዙ ቅርሶች ያሉባቸው በመሆናቸውና የሕዝቡ ባህል ሃይማኖታዊ ስለሆነ እነዚህ እንዳሉ ተጠብቀው እንዲቆዩ ሕዝቡን ለማጽናት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በዚህ አካባቢ ከወቅታዊ የተሃድሶ እንቅስቃሴ ጋር ተያይዞ ብዙ ፈተናዎች ይበዛሉ፤ ይህንንም በማስገንዘብ ምእመናን ራሳቸውንና ቤተ ክርስቲያናቸውን እንዲጠብቁ ነው ብለዋል፡፡

1600 ኪሎ ሜትር በሸፈነው ሐዋርያዊ ጉዞ የቀረቡት ትምህርቶችና መዝሙሮች በወቅታዊ የቤተ ክርሰቲያን ችግሮች ዙሪያ ያጠነጠኑ፥ ምእመኑ በሚረዳው ቋንቋ የቀረቡና ምእመኑ ለለውጥ የተነሳሳበት፣ ልዑካኑም ከምእመኑ የተማረበት ነበር ያሉት ቀሲስ ለማ በየጉባኤዎቹ መጨረሻ "ሕያው እውነት" መንፈሳዊ ፊልም መታየቱም የራሱ የሆነ ልዩ አስተዋጽኦ እንዳበረከተ ተናግረዋል፡፡

ምንም እንኳን ጉዞው በብዙው ስኬታማ ቢሆንም፥ ምእመናን የሰሟቸውን መዝሙሮች ለመገዛት ቢፈልጉም አለመመቻቸቱ፣ የጋዜጠኛ አብሮ አለመጓዝ፣ የካሜራ ባለሙያ አንድ መሆንና የመሳሰሉት ችግሮችን እንዳአስተዋሉ ቀሲስ አስታውቀው ለወደፊቱ መፍትሔ ሊበጅላቸው ይገባል ብለዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በዋና ክፍሉ ለሐዋርያዊ ጉዞ የሚያስፈልጉ ወጪዎችን በፕሮጀክት እየቀረጸ ለባለሀብቶች፣ በጎ አድራጊዎችና ለመንፈሳዊ ማኅበራት ያቀርባል፡፡ በእነዚህ አካላት ድጋፍ ሐዋርያዊ ጉዞ ያደርጋል፡፡ ለዚህኛውም ሐዋርያዊ ጉዞ 33,000 ያህል የወጣ ሲሆን በኢትዮጵያ አየር መንገድ ሠራተኞች መንፈሳዊ ጉባኤ 25,000 ብር ሲለግሱ  ቀሪውን ወጪ ደግሞ ማኅበሩን መሸፈኑ ታውቋል፡፡ 

ምእመናን

ለሐዋርያዊ ጉዞው መሳካት ከፍተኛውን ድርሻ የሚወስዱት አህጉረ ስብከቶቹ ናቸው ያሉት ቀሲስ ለማ የአህጉረ ስብከቶቹ ሊቃነ ጳጳሳት ከፍተኛ ቅስቀሳና መመሪያ በመስጠት፤ ሥራ አስኪያጆች፣ ልዩ ልዩ የመምሪያ ኃላፊዎችና የወረዳ ቤተ ክህነት ሊቃነ ካህናት በጉባኤ በመገኘት፣ የሚያስፈልገውን ሁሉ በማድረግ፣ ሕዝቡን በመቀስቀስ ከፍተኛ ቦታ መያዛቸውን ተናግረዋል፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑም ከጠዋቱ 11፡00 እስከ ሥራ ሰዓት መግቢያና ከሥራ መልስ በሰዓቱ በመገኘት ሥራውን ሳይፈታ ከትምህርቱም ሳይለይ የሚማር፣ ካህናቱም ሕዝቡን በመቀስቀስና የራሳቸውን አስተዋጽኦ በወረብና ቅኔ በማበርከት የተሳተፉበት ጉባኤ ነበር ብለዋል፡፡

ቀሲስ ለማ በጉባኤው ወቅት በማይጨው መካነ ሰማዕት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ባለው የሰማዕታት አፅም የሰማዕታት መታሰቢያ በዓል ለማክበር የመጡት ባለሥልጣናት ታዳሚ የሆኑበት፣ እኛም ለጊዜው ጉባኤውን አቁመን የአከበርንበት ሁኔታ ነበር ብለዋል፡፡

የሃገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ፣ የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ፣ የከተማው ከንቲባ፣ የአርበኞች ፕሬዝዳንት በአደረጉት ንግግር፣ ቤተ ክርስቲያን በሀገሪቱ የምታደርገውን እንቅስቃሴ አድንቀው ይሄ ዓይነቱ ጉባኤ የከተማውን መንፈሳዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ከሚያፋጥኑት ነገሮች አንዱ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ሐዋርያዊ ጉዞ ለቤተ ክርስቲያንዋም ሆነ ለሀገር ከፍተኛ አስተዋዕኦ የሚያበረክት ምዕመናንን በእምነታቸው እንዲጸኑ፣ ባህላቸውንና ቅርሳቸውን እንዲጠብቁ የሚያደርግ መንፈሳዊና ትውፊታዊ የጉዞ ጉባኤ ነው፡፡

 

 

 

በክለሳ ላይ ያለው የግቢ ጉባኤያት ሥርዓተ ትምህርት ትግበራው በ2004 ዓ.ም ይጀመራል ተባለ፡፡

 ዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ
 
ከ2000 ዓ.ም ጀምሮ እየተከናወነ ያለውን የግቢ ጉባኤያት የሥርዓተ ትምህርት ክለሳ በተመለከተ ከማዕከላትና ግቢ ጉባኤያት ተወካዮች ጋር ውይይት ተደረገ፡፡ ሥርዓተ ትምህርቱም ከ2004 ዓ.ም ጀምሮ ተግባራዊ እንደሚደረግ በማኅበረ ቅዱሳን የትምህርትና ሐዋረያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አስታወቀ፡፡

ከግንቦት 26 እስከ ግንቦት 27 ቀን 2003 ዓ.ም በተደረገው የውይይትና የምክክር መርሐ ግብር ከ11 ማዕከላት የመጡ የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ክፍል ኃላፊዎችና ከ15 ግቢ ጉባኤያት የተወከሉ ተማሪዎች የተሳተፉ ሲሆን ተወካዮቹ ከዚህ በፊት ይነሡ የነበሩ ችግሮች በክለሳውና በዳሰሳ ጥናቱ መታየቱ እንዳስደሰታቸው ገልጸው ለተግባራዊነቱ መፋጠን ይኖርብናል ሲሉ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡
የክፍሉ አስተባባሪ ቀሲስ ታደሰ ጌታሁን እንደገለጡት ክለሳው የተሠራው በ2000 ዓ.ም የተካሄደውን የዳሰሳ ጥናት መሠረት በማድረግ መሆኑን ገልጸው፣ ይህም የዳሰሣ ጥናት ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች፣ ለመምህራን ለክፍሉ አባላት መጠይቆችን በመበተን፣ ቃለ መጠይቅ በማድረግ፣ በአካል ቅኝት በማድረግና በመሳሰሉት እንደተከናወነ አስታውቀዋል፡፡
እስከ አሁን ሲተገበር የነበረው ሥርዓተ ትምህርት ለማኅበሩ የመጀመሪያ በመሆኑ ወጥነትና አንዳንድ መሟላት ያለባቸው ነገሮች ሳይሟሉ ተግባራዊ እንደሆነ የገለጹት አስተባባሪው አሁን እየተከለሰ ባለው ግን አንድ ሥርዓተ ትምህርት ሊያሟላ የሚገባውን አሟልቷል ብለን እናምናለን፡፡ ማኅበሩም ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ምን ዓይነት ፍልስፍና መከተል አለበት የሚለው ግንዛቤ ውስጥ ገብቷል፡፡ በተለይም ወደ ግቢ ጉባኤያት እየገባ ካለው ትውልድ አንጻር ሥርዓተ ትምህርቱ ሰፊ ፍተሻ እንደተደረገበትና ለሙከራም ከሚቀጥለው ዓመት ጀምሮ እንደሚተገበር አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን ከ1996 ዓ.ም ጀምሮ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለሚያስተምራቸው የገቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ሥርዓተ ትምህርት በመቅረጽ 20 መማሪያ መጻሕፍትን በማዘጋጀት እያስተማረ እንደሚገኝ ቀሲስ ታደሰ አስታውሰው በሚሰጡ ትምህርቶች ድግግሞሽና መሳሳብ እንደሚስተዋል፣ ለትምህርቶቹ የተመደበላቸው ሰዓቶች ከሚሰጡት ትምህርቶች አንጻር የማይመጣጠኑ እንደነበር በዳሰሳ ጥናቱ ወቅት እንደችግር ጎልተው እንደታዩ ጠቅሰዋል፡፡ ከክለሳው በኋላ የነበሩት 20 ትምህርቶችም ወደ 8 ዝቅ ማለታቸውን ያወሱት ቀሲስ ታደሰ በተጨማሪም ሦስት አዳዲስ ትምህርቶች ታክለዋል፡፡ እነዚህም ትምህርተ ክርስትና መግቢያ፣ ትምህርተ አበውና ልሳነ ግዕዝ እንደሆኑ ገልጸዋል፡፡
ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የሚሰጡ የትምህርት ዓይነቶችም ተማሪዎቹ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የቆይታ ጊዜያቸው የሚወሰን ሲሆን ለእያንዳንዱ ትምህርት ተመጣጣኝ ሰዓት፣ መለያ ቁጥር፣ ቅደም ተከተል እንዲሁም የትኛው የትምህርት ዓይነት ለማን ይሰጥ የሚሉ ጉዳዮች በቀጣይ የሚወሰኑ ናቸው፡፡
በሥርዓተ ትምህርቱ ክለሳ ፕሮጀክት መሠረት አዲሱ ሥርዓተ ትምህርት በዚህ ዓመት ተግባራዊ መሆን አልነበረበትም ወይ? ተብለው የተጠየቁት ቀሲስ ታደሰ ሲመልሱ ፕሮጀክቱ ከተጠበቀው በላይ ጊዜ የሚጠይቅ መሆኑንና በክለሳው የተሳተፉት ባለሙያዎች በሥራ መደራረብ ምክንያት ወደ ትግበራ መግባት እንዳልተቻለ ተናግረዋል፡፡ ቢሆንም ግን በ2004 ዓ.ም በተመረጡ ግቢ ጉባኤያት የሙከራ ትግበራ እንደሚጀመር አሳውቀዋል፡፡
ይህንን ሥርዓተ ትምህርት ከግብ ለማድረስ የግቢ ጉባኤያትና የማዕከላት ሥራ አስፈጻሚ አካላትን ግንዛቤ ማስጨበጥ እንዲሁም በቂ መምህራንን ለማፍራት ሥራ እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
አስተባባሪው እንዳሉት ከሥርዓተ ትምህርት ጋር ተዛማጅ ሙያ ያላቸው አባላት ክለሳውን አጠናቆ ትግበራ ለመጀመር እንዲያስችል በትምህርትና ሐዋረያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል በመገኘት በሙያቸው ተሳትፎ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን በቅዱስ ሲኖዶስ በጸደቀለት መተዳደሪያ ደንብ መሠረት ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ሥርዓተ ትምህርት ቀርጾ ተግባራዊ ካደረገ 7 ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ይህ ሥርዓተ ትምህርት ከተተገበረ ከ4 ዓመት በኋላ የዳሰሳ ጥናት በማድረግ የማኅበሩ ሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ 7 አባላት ያሉት ኃይለ ግብር አቋቁሞ ከ2001 ዓ.ም ጀምሮ የክለሳ ሥራው እየተከናወነ ይገኛል፡፡ 
hawire_Hiwot2.jpg

ከ 3000 በላይ ምዕመናን ይሳተፉበታል ተብሎ የሚጠበቅ መንፈሳዊ ጉዞ ተዘጋጀ

በተ/ሥላሴ ፀጋ ኪሮስ

ሰኔ 15 ቀን 2003 ዓ.ም

ከ6 ወራት በፊት ተዘጋጅቶ እንደነበረው በርካታ ምእመናን የሚሳተፉበት መንፈሳዊ ጉዞ ተዘጋጀ፡፡ ሐዊረ ሕይወት ቁጥር 2 የሚል ስያሜ ያለው ይህ ጉዞ ሰኔ 19 ቀን 2003 ዓ.ም ይከናወናል፡፡

hawire_Hiwot2.jpg

ከአዲስ አበባ 108 ኪ.ሜ ርቆ ፍቼ ከተማ ወደ ሚገኘው መካነ ሰማዕት አቡነ ጴጥሮስ ገዳም የሚደረገው ይህ ጉዞ መንፈሳዊ ሕይወታችን የምናጠነክርበት ይህም ከሆነ ዘንድ በቤተ ክርስቲያን የእኛ ድርሻ ምንድን ነው? ብለን ራሳችንን እንድንጠይቅና ኃላፊነታችንን እንድንወጣ የሚያስችል እንደሆነ የጉዞው አስተባባሪ ቀሲስ አንተነህ ጌጡ ተናግረዋል፡፡

ሐዊረ ሕይወት ምእመናን ከመኖሪያና ከሥራ ቦታቸው ራቅ ብለው በተሰበሰበ ልቡና የቅዱሳን ሰማዕታትና የጻድቃን በረከት በሚገኝበት ቦታ ተረጋግቶ ራስን እንዲያዩ የሚያስችል፣ የአበውን ተጋድሎ በመመልከትና በማስታወስ ከፍ ወደ አለ ሥነ ልቡና የሚያደርስና የቤተ ክርስቲያንን ጣዕም የሚያሳይ መንፈሳዊ ጉዞ እንዲሆን ታስቦ እየተዘጋጀ እንደሆነ በአስተባባሪዎቹ ተያይዞ ተገልጿል፡፡

በኢትዮጵያ አንድና ብቸኛ ወደ ሆነው የአቡነ ጴጥሮስ ገዳም በሚደረገው ጉዞ በሐዊረ ሕይወት ቁጥር አንድ ጉዞ ወቅት ተነስተው ላልተመለሱና አሁንም ለሚነሱ ጥያቄዎች ሰፋ ባለ ሁኔታ በአበው ሊቃውንት መልስ የሚሰጥበት የምክረ አበውን ዝግጅት በድጋሚ አካቷል፡፡ ባለፈው ከነበሩ መምህራንና ሊቃውንት በተጨማሪም ሌሎች በርካታ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የሚገኙበት እንደሆነ ተገልጿል፡፡ በተለይም ይህ ጉዞ የቤተ ክርስቲያንን ችግር ተረድተን መፍትሔ ፍለጋ ለመሄድ አቅጣጫ የሚሰጥ እንደሆነ አጽንኦት ተሰጥቶበታል፡፡

“ገዳሙ አንድና ብቸኛ መሆኑና ከአካባቢው ምእመናን በስተቀር በብዙው ኅብረተሰብ ዘንድ አይታወቅም በአሁኑ ጉዞ ወደ 3000 ምእመናን ይዘን እንጓዛለን ብለን እናስባለን” ያሉት ቀሲስ አንተነህ የሄዱት ምእመናን ለሌሎች ስለሚያስተላልፉ ገዳሙን በቀላሉ ማስተዋወቅ ይቻላል፡፡ በዚህም ምዕመናን የራሳቸውን አስተዋጽኦ ለገዳሙ እንዲያበረክቱ ያደርጋል ሲሉ ሌላኛውን አላማ ተናግረዋል፡፡

ሰማዕቱ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ሊቀ ጳጳስ ዘምሥራቅ ኢትዮጵያ የኢጣሊያ ጦር ሀገራችን ኢትዮጵያን በወረረበት ወቅት አርበኞችን በማስተባበር በጀግንነት ያዋጉ ሲሆን በጦርነቱ መሃል ተይዘው ስለሃይማኖታቸው በመመስከር የሀገራቸውን መሬትም ለፋሽስት እንዳትገዛ በመገዘት ሐምሌ 22 ቀን 1928 በሰማዕትነት ያረፉ አባት ናቸው፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በ2001 ዓ.ም በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ የቅድስና ማዕረግ ሰጥታ ጽላት ተቀርጾላቸው እንዲሁም በስማቸው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን በትውልድ ሀገራቸው ሰርታ ሰማዕተ ጽድቅ ዘኢትዮጵያ እያለች ታከብራቸዋልች፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ለምዕመናን መንፈሳዊ ሕይወት መጠንከር ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን የጠበቁ የተለያዩ መንፈስዊ ጉዞዎችን እንደሚያዘጋጁ የገለፁት ቀሲስ አንተነህ በቅርብ ጊዜ የአዲስ አበባ ማዕከል ባዘጋጀው መንፈሳዊ ጉዞ ከ3000 በላይ ምእመናንን የማኅበረሩን አባላት ሌሎች ማኅበራችንና ሰንበት ትምህርት ቤቶችን ይዞ ወደ ደብር ቅዱስ ደብር ጽጌ ማርያም ገዳም ያደረገውን የሐዊረ ሕይወት ቁጥር አንድ ጉዞን ተጠቃሽ አድርገዋል፡፡

የግቢ ጉባኤያትን ተማሪዎች መንፈሳዊ ሕይወት ለማሳደግ የሚያስችል የንሰሐ አባቶች ሴሚናር ተካሔደ

በእንዳለ ደጀኔ

ሰኔ 10 ቀን 2003 ዓ.ም 

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን በሰንበት ት/ቤቶች ማ/መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን መንፈሳዊ ህይወት ለማሳደግ የሚያስችል የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የንስሐ አባቶች ሴሚናር ተካሔደ፡፡
ከግንቦት 24 እስከ ግንቦት 26 ቀን 2003 ዓ.ም አዲስ አበባ ላይ በተካሔደው የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የንሰሐ አባቶች ሴሚናር በመላ ሀገሪቱ የሚገኙ ግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የንስሐ አባቶች ተወካዮች የተሳተፉ ሲሆን፥ በሴሚናሩም በቤተክርስቲያን ወቅታዊ ሁኔታ የንስሐ አባቶች ሚና፣ ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች መንፈሳዊ እድገት የንስሐ አባቶች ሚና፣ ሉአላዊነት ዘመናዊነት በተለይ ከአንቀጸ ንስሐ አንፃር፣ የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ተሞክሮ ወጣቶችን ለቤተክርስቲያን አገልግሎት ከማዘጋጀት አንፃር እና የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት ግቢ ጉባኤያትን ለቤተክርስቲያን አገልግሎት ከማዘጋጀት አንፃር የሚሉ ርዕሰ ጉዳዮችን መሠረት ያደረገ ነበር፡፡

ለመጀመሪያ ጊዜ በተዘጋጀው በዚህ የግቢ ጉባኤያት የንስሐ አባቶች ሴሚናር ቁጥራቸው 50 የሚደርሱ አባቶች መሳተፋቸው ታውቋል፡፡

በካህናቱ አቀባበል ላይ የተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም «እናንተን አባቶች እዚህ ድረስ እንድትመጡ ያስቸገርነው በግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች አገልግሎት ያላችሁ ድርሻ ታላቅ በመሆኑ ነው» ብለዋል፡፡

በሴሚናሩ ላይም ብፁዕ አቡነ ዮናስ የአፋር ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ እና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ተገኝተው ቡራኬና ቃል ምዕዳን የሰጡ ሲሆን «ማኅበሩ የሚያደርገው የልጅነት ድርሻውን በማገዝ እናንተ ካህናት ትልቁን ድርሻ ትይዛላችሁ» ብለዋል፡፡

ለ3 ቀናት በተካሔደው በዚህ ሴሚናር «እጅግ በጣም ተደስተናል» ያሉት ተሳታፊ ካህናቱ «ቀጣዩን ትውልዱ በመቅረጽና ለሀገርና ለቤተክርስቲያን ብቁና በሥነ-ምግባር የታነፁ ለማድረግ የምንችልበትን ግንዛቤ አግኝተናል። ይህም ካህናት ባገኘነው ግንዛቤና ልምድ ተነሳስተን ውጤታማ ሥራዎችን እንሰራለን» ብለዋል፡፡

ሴሚናሩም ሊቃውንቱን እርስ በእርስ ያስተዋወቀና በመረጃም ረገድ ልምድ ለመለዋወጥ መነሳሳትን እንደፈጠረላቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡

hohitebirhan.jpg

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተሐድሶ እንቅስቃሴ አለን? ዓላማውና ስልቱስ ምንድን ነው?

ሰኔ 11 ቀን 2003 ዓ.ም

/ምንጭ፦ ስምዐ ጽድቅ ልዩ እትም ግንቦት 2003 ዓ.ም/

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን “መታደስ አለባት” የሚሉ ድምፆችን የሚያሰሙ አካላት አሳባቸውን በተለያዩ መንገዶች ማሰማት ከጀመሩ ውለው አድረዋል፡፡ እነዚህ አካላት በመጽሔቶች፣ በጋዜጦች፣ በመጻሕፍት፣ በበራሪ ወረቀቶች፣ በዓውደ ምሕረት ስብከቶችና በሚያገኟቸው አጋጣሚዎች ሁሉ ይኸን ጩኸታቸውን ማስተጋባቱን ተያይዘውታል፡፡ እንዲህ እያሉ ያሉትም “ኦርቶዶክሳውያን ነን” እያሉ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ በተለያየ ቦታና ሓላፊነት ላይ ካሉና እንጀራዋን ከሚበሉ፣ ጥቂቶች እንዲሁም ደግሞ በኅቡእና በግልጽ በተለያየ መልክና ቅርጽ ራሳቸውን አደራጅተው ቤተ ክርስቲያኗ ሳትወክላቸው እርሷን ወክለው፣ “እኛም ኦርቶዶክስ ነን” በሚል ካባ ራሳቸውን ደብቀው እምነቷንና ሥርዓቷን “ይህ ሳይሆን ሌላ ነበር” እያሉ ፕሮቴስታንታዊ ትምህርትና መንፈስ የተዋረሳቸው ሰዎች ናቸው፡፡

 
ተሐድሶ የሚባል ነገር አለን? እነዚህ አካላት በአንድ በኩል ተሐድሶ የሚባል ነገር እንደሌለና ተሐድሶ የሚባለው ጉዳይ የሆነ አካል (እነርሱ እንደሚሉት ማኅበረ ቅዱሳን) ስም ለማጥፋት ሲል የፈጠረው የፈጠራ ወሬ እንጂ በሕይወት የሌለ ምናባዊ ነገር እንደሆነ ያስወራሉ፣ ይናገራሉ፡፡ ግን በእውነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዶግማዋ፣ ቀኖናዋና ትውፊቷ መታደስ አለበት በማለት የሚሠራ የተሐድሶ እቅስቃሴ የለምን?

ይህን ጉዳይ እነርሱው በይፋ ካወጧቸው የኅትመት ውጤቶቻቸው ለመመልከትና ለመታዘብ ይረዳ ዘንድ ራሳቸው በተለያዩ መጻሕፍቶቻቸው፣ መጽሔቶቻቸውና ጋዜጦቻቸው ካወጧቸው መካከል የተወሰኑትን ብቻ እንመልከት፡-

hohitebirhan.jpg

“እንደ እውነቱ ከሆነ በወንጌል እውነት ከታደሱ በኋላ በየጊዜው እየተመዘዙ የወጡት ምእመናኖቿና አገልጋዮቿ በውስጧ ቆይተው የተሐድሶን ሥራ እንዲሠሩ ቢደረግ ኖሮ፣ በወንጌል ተሐድሶ ያገኙ ክርስቲያኖች ለዓመታት የጸለዩበትንና የጓጉለትን የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተሐድሶ በቅርብ ጊዜ ሊያዩ ይችሉ እንደ ነበር የሚያምኑ ጥቂቶች አይደሉም፡፡” (ኆኅተ ብርሃን፣ መጋቢት 2002፣ ገጽ 15)

 


“ተሐድሶ እንቅስቃሴ በመሆኑ፣ እንቅስቃሴም ውጤታማና ትርፋማ ይሆን ዘንድ ዓላማን፣ ሒደትንና ግብን የያዘ ድርጊት እየተከናወነበት ያለ ሊሆን ስለሚገባው፣ ያለፈውና እየሆነ ያለው ግብረ ተሐድሶ ተመዝግቦ ለአሁኑና ለሚመጣው ትውልድ በሥነ ጽሑፍ ዳብሮና አምሮ ሊቀርብለት ይገባዋል፡፡” (ኆኅተ ብርሃን፣ መጋቢት2002፣ ገጽ 17) “በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ገብተን አረሞችን በገሀድ ካልነቀልን ተሐድሶን እንዴት ልናመጣ እንችላለን? መባሉ አይቀርም፡፡ ዳሩ ግን ስሕተቶችን ፊትለፊት ሳይቃወሙ ስሕተቶች እንዲታረሙ ማድረግ የሚቻልባቸው የተፈተኑ መንገዶች አሉ፡፡ ለምሳሌም …” (ኆኅተ ብርሃን፣መጋቢት 2002፣ ገጽ 19)

metkie.jpg


“ከ2000 ዘመናት በላይ ያስቆጠረች የእኛ ቤተ ክርስቲያንማ እንዴት አብልጦ ተሐድሶ (መታደስ) አያስፈልጋት?” (መጥቅእ፣ ኅዳር 2002፣ ገጽ 15) “ቤተ ክርስቲያናችን በክፉ ሰዎች ሴራ ዓላማዋን ስታለች፣ የሐዋርያትንም ትምህርት ገፍታለች፣ ስለ ሆነም ይህን የሐዋርያት ትምህርት በክፉዎች ምክንያት በመጣሱ በድፍረት ተሳስተሻልና ታረሚ ልንላት፣ በድፍረትም በሥልጣንም ሕዝቡን ልናስተምር ይገባል፡፡” (መጥቅእ፣ ኅዳር 2002፣ ገጽ 20) “ቤተ ክርስቲያናችን በየሀገሩ የተነሣውን የተሐድሶ የወንጌል እሳት በተለይ በሐረር፣ በባሕር ዳር፣ በአዲስ አበባ፣ በማርቆስ፣ በጎንደር፣ በሰሜን ሸዋ፣ በወሎ፣ በትግራይ፣ በባሌ ለማዳፈን ያን ሁሉ እልፍ አእላፍ ሠራዊት የቤተ ክርስቲያን አለኝታ ወጣት ወንጌል ባልገባቸው ምእመናንና ካህናት እያስደበደበች ለሌላ ድርጅት አሳልፋ ከመስጠት ይልቅ ስሕተቷን አርማ ልጆቿን በጉያዋ ብትይዝ ኖሮ ዛሬም ጭምር ጋብ ላላለው ፍጥጫ አትዳረግም ነበር፡፡” (መጥቅእ፣ ኅዳር 2002፣ ገጽ 16) “ሕዝባችን በልማድና በባህል ሃይማኖትን መያዙና ይህን የያዘውን ሃይማኖት ለመጣልና ለማጣራትም በቂ እውቀት ስለሚጎድለው በራሱ አንብቦ መረዳት ስለማይችል …” (የሚያሳውቁት ሃይማኖትን ለማስጣል ነው ማለት ነው) (ይነጋል፣ 1997፣ ገጽ 144)

 


እነዚህ እነርሱው ከጻፏቸውና አሳትመው ካሰራጯቸው መካከል ለአብነት ያህል የተጠቀሱት በግልጽ የሚያሳዩን ነገር ቢኖር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን እምነትና ትምህርት የሚቃወሙና ሊለወጥ ይገባል የሚሉ ራሳቸውን “ተሐድሶ” የሚል ስያሜ ሰጥተው በተለየ መልክና ቅርጽ በግልጽና በኅቡእ እየሠሩ ያሉ አካላት መኖራቸውን ነው፡፡ ራሳቸው እንዲህ በይፋ “እኛ አለን፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስ ቲያን ተሐድሶ ያስፈልጋታል” እያሉ እየተናገሩ “አይ፣ ተሐድሶ የሚባል ነገር የለም” ማለት እንዴት ይቻላል?

ዓላማቸው ምንድን ነው? ተሐድሶዎች ዋና ዓላማቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ዶግማ፣ ቀኖናና ትውፊት በመለወጥ ፕሮቴስታንታዊ ይዘት እንዲኖረው ማድረግ ነው፡፡ ምእራባውያን ሚሲዮናውያን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አጥፍቶ ፕሮቴስታንታዊ ለማድረግ መሥራት ከጀመሩበት ከሃያኛው መቶ ዓመት መጀመሪያ አንሥቶ እስከ አሁን ድረስ ሦስት ስልቶችን ተጠቅመዋል፡፡ የመጀመሪያው እስከ 1950 ዓ.ም ድረስ የሠሩበት ስልት ሲሆን እርሱም የራሳቸውን አስተምህሮ ማስተማር ነበር፡፡

ከ1950 ዓመት ጀምሮ እስከ 1990 ዓ.ም ድረስ ደግሞ የሠሩት የራሳቸውን እምነት መሰበክ ሳይሆን በዋናነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን በመንቀፍና በማጥላላት ምእመኑ እንዲኮበልል በማድረግ ነበር፡፡

ከ1990 ዓ.ም ጀምሮ እስከ አሁን እየሠሩበት ያለው ሦስተኛው ስልት ደግሞ "ኦርቶዶክስ ነኝ" ብሎ ውስጧ ገብቶ “ትታደስ” እያሉ በመጮኽ ቤተ ክርስቲያኗ እንዳለች እንድትለወጥ በማድረግ ምእመናኗን ከእነ ሕንፃዋና አስተዳደራዊ መዋቅሯ መረከብ ነው፡፡ የእነርሱ ምኞትና እቅድ የኢትዮጵያን ቤተክርስቲያን ወደ ሦስተኛው ሺሕ እንዳትሻገር ማድረግ ነበር፡፡ ነገር ግን እንዳሰቡት አልሆነም፡፡ በዚህም ብስጭታቸውን በተለያዩ ሚዲያዎች ገልጸዋል፡፡ ለምሳሌም ፓውልባሊስኪ (Paul Balisky) የተባለ “የዓለም አቀፍ ተልእኮ ማኅበር” የኢትዮጵያ ዳይሬክተር በ1992 ዓ.ም በወጣው “የክርስቲያን ሳይንስ ሞኒተር” በተባለ መጽሔት በሰጠው ቃለ መጠይቅ የደከሙት ድካምና ያወጡት ገንዘብ ሁሉ ወደ ጠበቁት ግብ እንዳላደረሳቸው፡-

“ይህ ሁሉ ጥረት ቢደረግም ወንጌላውያኑ አሁን በማደግ ላይና በመካከለኛ ኑሮ ላይ ያለውን የከተማውን ኅብረተሰብ መቀየር አልቻሉም፡፡ ምክንያቱም የተማረና ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ከፍተኛ ቅንዓት ያለው የወጣቶች ኃይል ማኅበረ ቅዱሳን የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በሃያ አንደኛው መ/ክ/ዘመን ዘልቃ መጓዝ ትችል ዘንድ እየተጋደለ ነውና፡፡” በማለት ከሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን በፊት የማጥፋት ሕልም እንደነበራቸው ገልጸዋል፡፡(The Christian Science Monitor, 8 June, 2000)

ስለሆነም ከዚያ በፊት ያደርጉት እንደነበረው በውጭ ሆኖ ምእመናንን ለመንጠቅ በመሥራት ብቻ ካሰቡት ቤተ ክርስቲያኒቱን ሙሉ በሙሉ የማጥፋት ግብ ለመድረስ ቀላል እንዳልሆነ ተረዱ፡፡ ስለዚህ አዲስ ስልት መቀየስ አስፈለጋቸው፡፡ ይህም “እናድሳለን”

በሚል ሽፋን ከውጭ ወደ ውስጥ ሠርጎ በመግባት ምእመኑን እስከ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑ የመረከብ ስልት ነው፡፡ ይህንም ኬንያ ውስጥ የሚታተመው “The Horn of Africa, Challe nge and opportunity” የተባለው መጽሔት “ዓላማው አዲስ ቤተ ክርስቲያን መመሥረት አይደለም፤ ቤተ ክርስቲያኗን (ኦርቶዶክስን) መለወጥ (ፕሮቴስታንት ማድረግ) እንጂ – The objective is not to set up a new church as such but to introduce reforms within the church” በማለት ገልጾ ነበር፡፡ (The Horn of Africa, Challenge and opportunity, p. 6)

ስለዚህ አዲሱ ስልት “የጥንቷ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ትክክል ነበረች – The ancient orthodox was the right Church” የሚል ነው፡፡ ይህም ማለት ቤተ ክርስቲያንን ከውጭ ከመቃወም ይልቅ ውስጥ ገብቶ ምእመን፣ ካህን፣ መነኩሴ፣ ሰባኪ … መስሎ ከፕሮቴ ስታንት እምነትና ባህል ውጭ ያለውን ነገር ሁሉ “ይህ የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን ትምህርት አይደለም፣ ይህን እገሌ የጨመረው ወይም የቀነሰው ነው … ’ እያሉ ቤተ ክርስቲያኗ ኦርቶዶክሳዊ ዶግማዋ፣ ቀኖናዋና ትውፊቷ በሙሉ ጠፍቶ ሙሉ በሙሉ ፕሮቴስታንት እስክትሆን ድረስ መሥራት ነው፡፡

ይህን ስልታቸውንም በኅትመቶቻቸው በይፋ ገልጸዋል፡፡ ለምሳሌም በአንድ ስልታቸውን ይፋ ባደረጉበት መጽሔታቸው ላይ እንዲህ ብለዋል፡-

“ታዲያ እርሷን (የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን) የማዳኑ ሥራ ከየት ይጀምር? እዳር ሆኖ አንዳንድ ምርኮኛን ማፍለሱ የሚፈለገውን የኦተቤን ተሐድሶ ሊያመጣ ይችላልን? አገልግሎቱ ከየት ወደ የት ቢሄድ ይሻላል? ማለት ከውስጥ ወደ ውጭ ወይስ ከውጭ ወደ ውስጥ? በውስጧ እያሉ የወንጌል እውነት ለተገለጠላቸው አገልጋዮቿ እንደ ውጊያ ቀጠና እግዚአብሔር የሰጣቸውን ምሽግ በአሁኑ ጊዜ የማስለቀቅና የጠላትን ወረዳ ከጥቃት ነጻ የማድረግ ሥራ እየተሠራ ያለው በሁለት ወገን ነው፤ … ” ይልና ቀጥሎም ወደ ግባቸው ለመድረስ መደረግ አለበት ያሉትን እንዲህ ዘርዝረዋል፡-

ውስጥ ያሉት እግዚአብሔር በሰጣቸው የውጊያ ቀጣና ውስጥ ሆነው በታማኝነት በእግዚአብሔር ቃል ምስክርነትና በጸሎት ውጊያውን መቀጠል አለባቸው፡፡ በውስጥ ላለው ለዚሁ ውጊያ በወንጌል የታደሱ ክርስቲያኖች ሁሉ እንደ ሙሴ እጃቸውን ወደ ላይ በማንሣት ታላቁን ርዳታ ማድረግና በደጀንነት መቆም ይገባቸዋል፡፡

እነዚህ በወንጌል ተሐደሶ አግኝተናል የሚሉ ሁሉ በውጭ ሆነው ወደ ውስጥ የሚያደ ርጉትን ውጊያ መቀጠላቸው እንደ ተጠበቀ ሆኖ ለውስጠኛው ውጊያ የሚያገለግል ትጥቅ ያላቸውን ወደ ውስጥ ማስገባትና የውስጠኛውን የውጊያ መስመር ማጠናከር ይጠበቅባቸዋል፡፡


“ … በዚህ የተቀናጀ ስልት መንፈሳዊው ጦርነት ቢቀጥል በውስጥ የተሰለፈው ሠራዊት (በተሐድሶ ስም የሚሠራው የፕሮቴስታንት ክንፍ) እያጠቃ ወደ ውጪ ሲገሰግስ፣በውጭ ያለውም (በግልጽ ፕሮቴስታንት ሆኖ የሚሠራው) ከበባውን አጠናክሮ ወደ ውስጥ ሲገፋ እግዚአብሔር በወሰነው ቀን የውስጡና የውጪው ሠራዊት ሲገናኙ በውስጧ የመሸገው ጠላት መሸነፉን በሚመለከት በአንድነት የድል ዝማሬ ሊያቀርቡ ይችላሉ፡፡”
(ኆኅተ ብርሃን፣ መጋቢት 2002 ዓ.ም)

ይህ ሁሉ የሚያሳየው

ሀ) በቤተ ክርስቲያኒቷ ላይ በይፋ የተቀናጀ ጦርነት ያወጁባት መሆኑን፣

ለ) የጦርነቱ አንዱ ስልት ውስጥ ሆኖ በውስጥ አርበኝነት መሥራትና መዋጋት መሆኑን፣

ሐ) የጦርነቱ ዓላማ ጠላት የተባለችውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማፍረስ መሆን ነው፡፡


የተሐድሶው ዘመቻ ዘዴዎች ምንድን ናቸው?

ተሐድሶዎች ያሰቡትን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን እንዳለች ፕሮቴስታንታዊ አድርጎ ለውጦ ለመረከብ ያላቸውን ምኞትና ዓላማ እውን ለማድረግ የተለያዩ ዘዴዎችን ይጠቀማሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል ሁለቱ የሚከተሉት ናቸው፡፡

ሀ) የሐሰት ውንጀላዎችን መፍጠርና ማሰራጨት ሌባ ሲሰርቅ የሚያየውን ወይም መስረቁን ያወቀበትን ሰው ይወዳል ብሎ ማሰብ ከባድ ነው፡፡ እንደዚሁም እነዚህ በውጫቸው የቤተ ክርስቲያንን ለምድ የለበሱ፣ በውስጣቸው ግን ኦርቶዶክሳዊ የሆነውን እምነትና ባህል አጥፍቶ የምእራባውያን ባህል ተሸካሚ ለማድረግ የሚሠሩ ክፉ ሠራተኞች (ፊል.3÷2) ዓላማቸውንና ስልታቸውን የሚያውቅባቸውን ማንኛውንም ግለሰብም ሆነ ማኅበር አምርረው ይጠሉታል፣ ይፈሩታልም፡፡፡ በእነ ማርቲን ሉተር በአውሮፓ ተካሒዶ ምእራባውያንን ወደ እምነት አልባነትና ክህደት ማድረሱን ዛሬ በተግባር ያስመሰከረውን ተሐድሶ (ፕሮቴስታንት) በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንም ላይ እውን በማድረግ ይሁዳ ስለ ሠላሳ ብሩ ሲል ጌታውንና አምላኩን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመሸጥ ከጸሐፍትና ከፈሪሳውያን ጋር “አሳልፌ እንድሰጣችሁ ምን ትሰጡኛላችሁ?” (ማቴ.!1÷05) ብሎ ጌታውን ለሽያጭ እንዳቀረበ፣ እነዚህም ስንቅና ተስፋ የሚሰጧቸውንና ስልት ነድፈው ከርቀት እያሳዩ የሚያሠሯቸውን የላኪዎቻቸውንና የጌቶቻቸውን ምኞት ለማሳካት እንቅፋት ይሆኑብናል የሚሏቸውን ሁሉ ማሩን አምርረው ወተቱን አጥቁረው በማሳየት ስማቸውን በማጥፋት እንዲጠሉ ለማድረግ ይሞክራሉ፡፡

ከዚህ ተግባራቸው ለምሳሌ ያህል ብንጠቅስ በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ በተሰጠው ሕገ ደምብ መሠረት በአባቶች ቡራኬና ፈቃድ የተመሠረተውንና በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር ሆኖ ዓቅሙ በፈቀደ መጠን ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዘርፈ ብዙ አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኘውንና ይህን ለቤተ ክርስቲያናችን እጅግ አደገኛ የሆነ የተሐድሶ እንቅስቃሴ ምንነት በማጋለጥ ለሕዝብ የሚያስረዳውን ማኅበረ ቅዱሳንን ስሙን በኅትመቶቻቸውና በልዩ ልዩ መንገድ ማጥፋትና ሰይጣናዊ አስመስሎ መሳል አንዱ ስልታቸው ነው፡፡ ለአብነት ያህልም የሚከ ተሉትን እንመልከት፡-


“ማቅ (ማኅበረ ቅዱሳን) ያለ እኔ ቤተ ክርስቲያን፣ ሀገርና መንግሥት የለም ብሎ በጭፍን የሚያስብ ስለሆነ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሌላ መንፈሳዊ ማኅበርም ሆነ ጉባኤ ለማየት ዓይኑ የተሸፈነ ነው፡፡ ራሱን የቅዳሴ፣ የቅኔና የመጻሕፍት ማስመስከሪያ ቤተ መምህራን አድርጎ በማየቱ በእርሱ እጅ ፈቃድ ያላገኙ ሰባክያንና መዘምራን ቢፈጠሩ የተለመደው የኮሚኒስቶች ፍልስፍና (የሀሰት ስም የማጥፋት ቅስቀሳውን) ያወርድባቸዋል፡፡”
(መጥቅእ፣ ኅዳር 2002፣ ገጽ 1፣ርእሰ አንቀጽ)

እንግዲህ ይህን የሚለው አካል በግልጥ ቤተ ክርስቲያኒቱ ተሐድሶ ያስፈልጋታል እያለ በዚሁ ጋዜጣ የገለጸው የተሐድሶ ድርጅት ነው፡፡ ልዩነቱ የዓላማ መሆኑን ራሳቸው ተናግረው ሲያበቁ እንደገና መልሰው ተሐድሶ መባልን የሐሰት ስም ማጥፋት ዘመቻ ነው ይላሉ፡፡ አንባቢዎቻቸው ይህን እንኳን ማገናዘብ አይችሉም ብለው ይሆን?

“የማኅበረ ቅዱሳን ትምህርት እግዚአብሔር ፍጹም ጨካኝ ስለሆነ ስለማይሰማንና በርኅራሄ ከእርሱ የተሻሉ ቅዱሳን በፊቱ ቆመው እንዲለምኑልን የእነርሱ ልመና ግድ ብሎት ስለሚምረን በአማላጅነት እንመን ይላል፡፡” (ይነጋል፣ 1997 ዓ.ም. ገጽ 123) “ማኅበረ ቅዱሳን የተባለው ይህ የሰይጣን ማኅበር አሁን ወደ ነፍሰ ገዳይነት ሊገባ ራሱን እያዘጋጀ ነው፡፡” (ይነጋል፣ 1997 ዓ.ም.ገጽ 127) ይህ የስም ማጥፋት ዘመቻ በሀገር ውስጥ ባሉ ሚዲያዎች ብቻ የተወሰነ ሳይሆን ዋናው የተሐድሶ ዘመቻ አርቃቂዎችና ስልት ነዳፊዎች በሆኑት በምእራባውያን ፓስተሮችም በብዛትና በዓይነት የሚሠራ ሥራ ነው፡፡ ለምሳሌ ያህልም ዊሊያም ብላክ የተባለው አሜሪካዊ ፓስተር አናሲሞስ በተባለው የጦማር መድረኩ ላይ የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን እንዴት ማፈራረስ እንደሚቻልና በአሁኑ ወቅትም የእርሱና መሰል ድርጅቶች ቤተ ክርስቲያንን እንዴት እየተዋጓት እንደሆነ “Struggle for the soul of the Ethiopian orthodox Church” በተሰኘው ጽሑፉ ላይ በሰፊው ገልጧል፡፡ የፕሮቴስታንት ጉዳይ አስፈጻሚ የሆነው የተሐድሶ አንቅስቃሴ ምን ማለት መሆኑን ለዓላማቸው መሳካት እንቅፋት ሆኖብናል ያለውን ነገር ሲናገር ገልጾታል፤ እንዲህ ሲል፡-

“Working against both the ongoing creep of Western values and the attempts by Reformists to restore the church, a reactionary movement called Mahebere Kidusan and led by members of the hierarchy and priests and others, are seeking to fend off any changes and to preserve aspects of the Church which they feel are crucial to their identity and Ethiopia’s place in the world. …

በሀገሪቱ ውስጥ እየተንሰራፋና ሥር እየሰደደ ያለውን ምእራባዊ ባህልና በተሐድሶ አራማጆች ቤተ ክርስቲያኒቷን ለማደስ የሚደረገውን ጥረት ሁለቱንም የሚቃወምና ለዚህም እየሠራ ያለ አድኃሪ የሆነ ማኅበረ ቅዱሳን የሚባል እንቅስቃሴ አለ፡፡ ይህ ማኅበርም ቤተ ክርስቲያንን ለመለወጥ የሚደረገውን ማንኛውንም ነገር ለመከላከልና ለራሳቸው ማንነትና ኢትዮጵያ በዓለም ስላላት ቦታ አስፈላጊ ነው የሚሉትን የቤተ ክርስቲያኒቷን ገጽታ ለመጠበቅ ይፈልጋሉ፡፡”

http://www.Compassdirect.org/english/country.ethiopia/11092/ተሐድሶዎች ቤተክርስቲያናቸውን የሚወዱትንና ለእምነታቸውና ለሥርዓታቸው ተቆርቋሪ የሆኑትን ምእመናን፣ ካህናት፣ መነኮሳት … ሁሉ ማኅበረ ቅዱሳን የሚባል ነገር መኖሩን ከነ ጭራሹ ያልሰሙ ሰዎች ቢሆኑም እንኳ “ማኅበረ ቅዱሳን (ማቅ)” ናቸው የሚል ታርጋ በመለጠፍ ለማሸማቀቅ ይሞክራሉ፡፡ በዚህም የተሐድሶ ጉዳይ የሌለና የሆኑ ቡድኖች ጠብና ሽኩቻ ብቻ ተደርጎ እንዲታይ ይጥራሉ፡፡ እጅግ በጣም ብዙ የሆኑ ለማመን የሚከብዱ የበሬ ወለደ ዓይነት የስም ማጥፋት ወሬዎችን በማኅበሩ ላይ በማሰራጨት ላይ ናቸው፡፡ ለምሳሌም በቅርቡ “የማኅበረ ቅዱሳን የሃያ አምስት ዓመት ስትራቴጂ ነው” በሚል ስም አንድን ሕፃን እንኳ ሊያሳምን በማይችል መልኩ ራሳቸው የፈጠሩትን አሉባልታ የማኅበሩ አስመስለው በሐሰት ማኅተም አትመው በኢንተርኔት አሰራጭተዋል፡፡ እንዲህ ዓይነት የፈጠራ ክሶችንና ስም ማጥፋቶችን ደህና አድርገው ተያይዘዋቸዋል፡፡

ለ) የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተዳደርና መዋቅር መቆጣጠር ተሐድሶዎች ቤተ ክርስቲያኒቷን ለመለወጥና ለዓላማቸው ማስፈጸሚያ የተመቸች ለማድረግ ይረዳቸው ዘንድ ለመቆጣጠር የሚመኙት አንዱ ነገር የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተዳደርና መዋቅር መያዝ ነው፡፡ ይህን ማድረግ ከቻሉ በቤተ ክርስቲያኒቱ አንደበት በመናገር፣ ቤተክርስቲያን ያልሆነችውን ናት፣ የሆነችውን ደግሞ አይደለችም በማለት ያሰቡትን የተሐድሶ ዓላማ ከግብ ለማድረስ ይረዳቸዋል፡፡

ወደዚህ ግብ ለመድረስም በተለያዩ ጊዜያትና ስልቶች ከመሪጌቶች፣ከቀሳውስት፣ ከመነኮሳት፣ ከዲያቆናትና ከሌሎችም መካከል በተለያየ ጥቅማ ጥቅምና ድለላ የማረኳቸውንና ያሰለጠኗቸውን ሰዎች በአስተዳደር መዋቅሩ ውስጥ ለማስገባትና ቦታውን ለመያዝ ደፋ ቀና በማለት ላይ ናቸው፡፡ በዚህም የተወሰነ ርቀት መጓዝ ችለዋል፡፡ ይህም በስልታቸው እንደ ገለጹት “መንፈሳዊ ቀውስ የደረሰበትን አስተዳደር ማረምና ማስተካከል” (ኆኅተ ብርሃን፣ መጋቢት2000፣ ገጽ 16) በሚል ሽፋን የሚካሔድ ነው፡፡

ይህን ጉዳይ እስከ የት ድረስ መግፋትና ማድረስ እንደሚፈልጉ ሲገልጹም እንዲህ ብለዋል፡-

“ማቅ (ማኅበረ ቅዱሳን) ወደደም ጠላም ቤተ ክርስቲያኒቱ በእውነት በሚወዷትና የወንጌልን እውነት በሚያገለግሉ መምህራንና ሊቃውንት ይህንም እውነት ተቀብለው አምላካቸውን በንጹሕ ልብ ሆነው በሚያመልኩ፣ በተለይም መጪው ዘመን በትካሻቸው ላይ የወደቀባቸው ከመንፈሳዊ ኮሌጆቻችን እየተመረቁ የሚወጡ የወንጌል አርበኞችና ቤተ ክርስቲያንን ይጠብቁ ዘንድ እግዚአብሔር ጳጳሳት አድርጎ የሾማቸው አባቶች በሚወስዱት የማያዳግም እርምጃ ቤተ ክርስቲያናችን ተሐድሶን ታደርጋለች፡፡” (መጥቅእ፣ ኅዳር 2000፣ ገጽ 2) ጳጳሳት ሳይቀሩ የማያዳግም እርምጃ መውሰዳቸውና ቤተ ክርስቲያኒቱን ማደሳቸው የማይቀር መሆኑን በግልጽ ተናግረዋል፡፡ ስለሆነም ይህን ሕልማቸውን እውን ለማድረግ የቤተ ክርስቲያኗን የአስተዳደር መዋቅር፣ እስከ ጵጵስና ደረጃ ያለውንም መቆጣጠር ዋና ስልታቸው ነው፡፡

ዛሬ የመነኮሱበት የማይታወቅ ሰዎች የአባቶቻችንን ቆብ አጥልቀው መስቀሉን ጨብጠው ቀሚሱን አጥልቀው ካባውን ደርበው፣ ያልሆኑትን መስለው፣ ሌሎችም የነበሩ፣ ዛሬ ግን ያልሆኑ፣ ዓላማቸውን እንደ ይሁዳ ለውጠው የክፋቱ ተባባሪ ሆነው ያሉ ሁሉ በቤተ ክርስቲያኗ ስም ሲጫወቱ ዝም እየተባሉ ስለሆነ እነዚህ ሰዎች የነገዪቱ ጳጳሳት የማይሆኑበት እድል አይኖርም ብሎ ማሰብ አይቻልም፡፡

ይልቁንም አሁን ሃይማኖታቸው በግልጽ ፕሮቴስታንት (ተሐድሶ) የሆኑና ብዙ ጉድ ያለባቸው፣ የምግባር ድቀት ያንገላታቸው፣ የሃይማኖት አባት ሆነው ምእመናንን ለማስተ ማርና ለመምራት ቀርቶ ተነሳሒ ለመሆን እንኳ የከበዳቸው ሰዎች ዓይናቸውን በጨው ታጥበው ጵጵስና ለመሾም የሲኖዶስ ስብሰባ በመጣ ቁጥር አፋፍ ላይ እየደረሱ እየተ መለሱ ነው፡፡ ይህ ሁኔታ እንዲሁ ከቀጠለ እነዚህ ሰዎች አንድ ቀን የጳጳሳትን አስኬማ ደፍተው፣ በትረ ሙሴ ጨብጠው፣ “አቡነ” እገሌ ተብለው ላለመምጣታቸው ምን ዋስትና አለ? “ሞኝ ቢቃጡት የመቱት አይመስለውም” እንደሚባለው እንደ እነዚህ ዓይነት ሰዎችን ለጵጵስና እጩ አድርጎ እስከማቅረብ ደረጃስ እንዴት ሊደረስ ቻለ?

ማንነታቸው ተጣርቶ በንስሐ የሚመለሱት ቀኖና ሊሰጣቸው፣ የማይመለሱት ደግሞ ሊለዩ (ሊወገዙ) ሲገባቸው የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ሆነው በቤተ ክርስቲኒያቱ ህልውና ላይ ወሳኝ አካላት ሊሆኑ መታሰቡ በራሱ የሚያሳየው ከባድ ነገር አለ፡፡

እነዚህን ሰዎች በአድባራትና በገዳማት ዕልቅናና በተለያየ ሓላፊነት ከመሾም ጀምሮ ግልጽ የሆነ የአደባባይ ጉዳቸውን ዝም ከማለትና አልፎ አልፎም ከማበረታታት ጀምሮ በቤተ ክርስቲኒያቱ አስተዳደር ውስጥ እንዳሻቸው እንዲናኙበት የሚፈቅድና የሚመች የተሐድሶ ሰንሰለት አለማለት ይሆን?

እውነተኛ የቤተ ክርስቲያን ልጆችና አባቶች እንደ እንጀራ ልጆች እየተቆጠሩና እየተገፉ እነዚህ ተሐድሶዎች ደግሞ ባለሟሎች መስለው ከዚያም አልፎ ለጵጵስና ታጭተው ማየትና መስማት በእጅጉ ያማል፣ ልብንም ያደማል፡፡ ስለዚህ እነዚህ ሰዎች አናት ላይ ወጥተው የጵጵስና መዓርግ ጨብጠው ከመጡ በኋላ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ ሊያመጡ ያሰቡትን ስልታዊ አደጋ መገመት ውኃን የመጠጣት ያህል ቀላል ነው፡፡

ስለሆነም እነርሱ ያሰቡት ከባድ ትርምስ ሳይመጣ ‹ሳይቃጠል በቅጠል› እንዲሉ በጊዜ ከጸሎት ጀምሮ ማንኛውም ሊደረግ የሚገባውን የመከላከል ሥራ ከወዲሁ መፈጸም ይገባል፡፡ ቁጭ ብሎ የሰቀሉትን ቆሞ ማውረድ ያቅታልና፡፡ ይህም “እነ እገሌ ምን እየሠሩ ነው?” በሚለው ያልጠቀመን ፈሊጥ ሳይሆን “እኔ ምን አደረግሁ?

አሁንስ ምን ማድረግ አለብኝ?” በሚል ሊሆን ይገባል፡፡ የቤተ ክርስቲያን አምላክ እግዚአብሔር በቤቱ የተሰገሰጉ ይሁዳዎችን የሚያጋልጥበትንና ከመንጋው የሚለይበትን ዘመን ያቅርብልን፣ አሜን፡፡

መልአከ ገነት ኃይለ ማርያም ፋንታሁን

መልአከ ገነት ኃይለ ማርያም ፋንታሁን አረፉ።

ከባህር ዳር ማእከል

ሰኔ 9 ቀን 2003 ዓ.ም

መልአከ ገነት ኃይለ ማርያም ፋንታሁንበባህር ዳር ከተማ በሚገኘው ፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳምን ከ40 ዓመት በላይ በአስተዳዳሪነት ያገለገሉት መልአከ ገነት ኃይለ ማርያም ፋንታሁን በጠና ከታመሙ በኋላ በተወለዱ በ80 ዓመታቸው ግንቦት 30 ቀን 2003 ዓ.ም ከምሽቱ 2፡00 ሰዓት አርፈዋል። 

ሥርዓተ ቀብራቸው ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ፣ ብፁዕ አቡነ ኤልያስና ብፁዕ አቡነ ቶማስ፣ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ እንዲሁም ወዳጅ ዘመድና ቤተሰቦቻቸው በተገኙበት በፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳም በዕለተ ሐሙስ ሰኔ 2 ቀን 2003 ዓ.ም ከቀኑ 5፡30 ተፈጽሟል፡፡

 
መልአከ ገነት ኃይለ ማርያም ከአባታቸው መምህር ፋንታሁን ጥሩነህ እና ከእናታቸው ወ/ሮ ውዴ አካሌ በምዕራብ ጎጃም ዞን በሜጫ ወረዳ በደብር መድኃኒት ማርያም ልዩ ስሟ ደረመኔ በተባለ ቦታ የተወለዱ ሲሆን እድሜያቸው ለትምህርት እንደደረሰ አባታቸው ተተኪ አገልጋዮችን ለማፍራት ባላቸው ልዩ ፍላጎት የተነሣ መንፈሣዊ ትምህርት ቤት በመግባት የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በትጋት በመማር እንዲሁ ደግሞ ወንበር ዘርግተው በማስተማር፣ ተተኪ ካህናትንና መምህራንን በማፍራት፣ ለከፍተኛ ማዕረግ የበቁ ጳጳሳትን በማፍራት፣ ከ300 በላይ መነኮሳትን አመንኩሰዋል። ከመነኮሱት ውስጥም ለፓትርያርክነት ማዕረግ የበቁ ያሉበት ሲሆን ፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳምን ለ43 ዓመታት በማስተዳደር፣ በቤተ ክርስቲያኒቷ የተለያዩ የልማት ሥራዎች ላይ በመሣተፍ፣ ችግረኞችን በመርዳት፣ የተጣሉትን በማስታረቅ፣ ያዘኑትን በአባታዊ ምክር የሚያረጋጉ አባት እንደነበሩ አጭር የሕይወት ታሪካቸው ያስረዳል።